ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዛሬዋ ቱርክ ኢያዞሎክ፣ በጥንታዊቷ የኤፌሶን ከተማ ተገኝቶ ነበር፡፡ በዚህች ከተማ እጅግ የታወቀች፣ ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች አማንያን የሚጎርፉላት፣ ምስሏን የሚሠሩ አንጥረኞች ብር በቁና የሚያተርፉባት አርጤምስ የምትባል ጣዖት ትመለክ ነበር፡፡ ጳውሎስ እዚህ ከተማ ገብቶ ወደ አርጤምስ ቤተ መቅደስ በመጓዝ ‹‹አርጤምስ አምላክ አይደለችም›› ብሎ አስተማረ፡፡

ይህን ሲሰሙ የአርጤምስ ወዳጆች፣ ምስሏን በመሥራት የሚያተርፉት አንጥረኞችና፣ አርጤምስን ለመሳለም ከሚመጡ አማኞች ጠቀም ያለ ትርፍ የሚያገኙ ነጋዴዎች በከተማዋ ሑከት አስነሡ፡፡ ከተማዋ ተደበላለቀች፡፡ ከየአቅጣጫው ሕዝቡ ወደ ቤተ መቅደሱ አደባባይ ጎረፈ፡፡ የሐዋርያት ሥራ እንዲህ ይላል፡፡ ‹‹ብዙዎች ወዲያና ወዲህ እያሉ ይጮኻሉ፡፡ በጉባኤው ድብልቅልቅ ሆኖ፣ የሚበልጡት ስለምን እንደተሰበሰቡ እንኳን አያውቁም ነበር፡፡››

አርጤምሳዊነት ባልተረዱት፣ ምስክርነት በማይሰጡበት፣ በማያውቁት ጉዳይ ላይ ሌሎች ስላደረጉት ብቻ፣ ወይም ደግሞ ሕዝቡ ሁሉ ሲያከናውነው ስለታየ ብቻ መደገፍ ወይም መቃወም፣ ወይም ያንኑ መሥራት ማለት ነው፡፡ የሚሰበሰቡበትን ምክንያት ሳያውቁ መሰብሰብ፣ የሚደግፉበትን ምክንያት ሳያውቁ መደገፍ፣ የሚቃወሙበትን ምክንያት ሳያውቁት መደገፍ፣ የሚወዱበት ምክንያት ሳይኖር መውደድ፣ የሚጠሉበትንም ምክንያት ሳይረዱት መጥላት ነው፡፡

ለምን? ሲባል ‹‹እኔ ከሰው እለያለሁ እንዴ›፣ ሰው ሁሉ እንዲህ እያደረገኮ ነው፣ መቼም አንድ ምክንያት አይጠፋም ብዬ፣ እነ እገሌ ሲሄዱ ሄድኩ፣ ዝም ብሎ ያስጠላኛል፣ እንዲሁ ጥሎብኝ እወደዋለሁ፤ ከሰው ጋር ሲኖሩ ሞኝ ሆኖ፣ አህያ ሲጭኑ ሦስት ሆኖ ስለሚባል፣ እየተባለ ዝም ብሎ መደገፍና መቃወም ነው አርጤምሳዊነት፡፡

መመሪያ ስለሆነ፣ አድርጉ ስለተባልን፣ አሠራር ነው፣ የተለመደ ነው፣ በኛ ጊዜ አልተጀመረም፣ ድሮም የነበረ ነው፣ ምን ይደረግ ታዝዘን ነው፣ እኔ ከማን እበልጣለሁ፣ እኔ ከማን አንሣለሁ፣ ከበላይ የመጣ ነው፣ ውጡ ስለተባልን ነው፣ የሚሉ ነገሮችን የምትሰሙባቸው መሥሪያ ቤቶች ካሉ እነዚህ መሥሪያ ቤቶች በአርጤምሳውያን የሚመሩ ወይም የተሞሉ ናቸው ማለት ነው፡፡ ይፈርማሉ፤ ለምን? ማብራራት አይችሉም፤ ይሰበሰባሉ፤ ለምን ተሰበሰባችሁ? ሳትሰበሰቡ ማድረግ አትችሉም ነበር ወይ? ሲባሉ ምክንያት ያለው መልስ የላቸውም፡፡ ይውደም ይላሉ፤ ማንን እንደሆነ አያውቁትም፡፡ ይቅደም ይላሉ ማን እንደሚቀድም ግን አልወሰኑም፡፡

አንዳንዶች ጓደኞቻቸው ያደረጉት፣ የተከተሉት፣ ያወሩት፣ የወደዱት፣ የጠሉት፣ የደገፉት፣ የተቃወሙት ሁሉ ትክክል ነው ብለው ያምናሉ፡፡ አመክንዮ የላቸውም፡፡ የተደረገውን ከመድገም በቀር፡፡ ከዚህም አልፈው ከራሳቸው አእምሮ ይልቅ በሰው አእምሮ ያስባሉ፡፡ ሌላውን ሰው መከተል እንጂ የት ይወስደኛል፣ ለምን አከተለዋለሁ፣ ትክክል ነው ወይ? እኔ የተሻለ ሃሳብ የለኝም ወይ? ብለው አይጠይቁም፡፡ እንዲሁ ይከተላሉ፡፡

አርጤምሳውያን ሰውን እንጂ ሃሳብን አይከተሉም፡፡ ሰውን እንጂ ሃሳብን አይቃወሙም፡፡ ለእነርሱ ቁም ነገሩ እነማን አሉበት? የሚለው እንጂ ምን ነገር አለበት? የሚለው አይደለም፡፡ አንድ ጊዜ አንድ ድልድይ ላይ ብዙ ሰዎች ተሰብስበዋል፡፡ ተሰብስበውም ወደ ድልድዩ ሥር ይመለከታሉ፡፡ እኔ ማዶ ቆሜያለሁ፡፡ ቀስ በቀስ ድልድዩ ላይ ቆመው የሚመለከቱት ሰዎች ቁጥራቸው እየበዛ መጣ፡፡ በኋላም በድልድዩ ላይ መኪና ማለፍ እስኪያቅተው ድረስ በሰው ተሞላ፡፡የምጠብቀው መኪና መጣልኝና በድልድዩ ላይ ለማለፍ ከሌሎች መኪኖች ኋላ ወረፋ ያዝን፡፡ መኪኖቹ በሕዝብ በተጣበበው ድልድይ ላይ እንደ ዔሊ እየተንፏቀቁ ነበር የሚጓዙት፡፡ እንዳጋጣሚ ሆኖ ነገሩ ሲጀመር አካባቢ ድልድዩ ላይ ያየሁትን ሰው አገኘሁትና የመስኮቱን መስተዋት አውርጄ ‹‹ምንድን ነው ጉዳዩ?›› ብዬ ጠየቅኩት፡፡

እጁን ኪሱ ውስጥ ከትቶ ትከሻውን እያራገፈ ‹‹የሆነ ነገር ሳይገባ አይቀርም›› አለኝ፡፡

‹‹አንተ አላየኸውም›› አልኩት፡፡

‹‹አላየሁትም፤ አንዳንዶች ከብት ነው ይላሉ፣ ሌሎቹ ደግሞ ሰው ነው ይላሉ›› አለኝ፡፡

‹‹አንተ ምን ትላለህ›› አልኩት

‹‹እኔ እንጃ›› አለ፡፡

‹‹ይህንን ካላጣራህ ታድያ ለምን መጣህ››  አልኩት

‹‹ሰው ሲሰበሰብ ጊዜ ዝም ብዬ ነው የመጣሁት›› አለኝ፡፡

ቢያንስ ከሠላሳ ደቂቃ በላይ ቆሟል፡፡ እንዲህ ሰው ሳይጨናነቅ ነበር የመጣው፡፡ የመጣበትን ምክንያት ግን አያውቀውም፡፡ ሰው ተሰበሰበ፣ እርሱም አብሮ ተሰበሰበ፡፡ ሰው ወደ ድልድዩ ሥር ያያል፤ እርሱም ያያል፡፡ ምን እንደሚያይ ግን አያውቅም፡፡ ብቻ ያያል፡፡ አርጤምሳዊ፡፡

አርጤምሳውያን ነገሩ ሳያስቃቸው ነው የሚስቁት፡፡ የተሰበሰበው ሰው ከሳቀ ይስቃሉ፡፡ ቀልዱ ግን ላይገባቸው ይችላል፡፡ ባይገባቸውም ያጨበጭባሉ፡፡ ከዐዋቂ መካከል ከተቀመጡም ራስ ሲነቀነቅ ሲያዩ ይነቀንቃሉ፡፡ የሆነ ወረቀት ሲታደል ካገኙ ይቀበላሉ፤ ግን አያነቡትም፡፡ ማስተዋሻ ሲሰጥ ካዩ ተስገብግበው ይወስዳሉ፤ ግን አይጽፉበትም፡፡ የሆነ ምዝገባ ነገር ከተመለከቱ ወደ ሲኦል ለመሄድ ቢሆን እንኳን አያጣሩም፤ ብቻ ይመዘገባሉ፡፡ የሆነ ኮሚቴ፣ ማኅበር፣ ቡድን ሲመሠረት ዘለው ይገባሉ፤ ዓላማው፣ አሠራሩ፣ ማንነቱ አይመለከታቸውም፡፡ ዓላማቸው መቀላቀል ብቻ ነው፡፡

ኢሜይል አላቸው፣ የሚገናኙት ሰው የለም፤ ፌስ ቡክ አላቸው የሚለጥፉት ነገር የለም፡፡ ትዊተር አላቸው፣ የሚያስተላልፉት ነገር የለም፡፡ በሞባይላቸው ይቀዳሉ፣ እነርሱስ ከማን ያንሳሉ፡፡ ግን የቀዱትን አያዳምጡትም፡፡ እንዲያውም በቀጣዩ ደምስሰው ሌላ ይቀዱበታል፡፡ በሞባይል ፎቶ ያነሣሉ፤ ደግመው ግን አያዩትም፡፡ አርጤምሳውያን፡፡

አርጤምሳውያን ቤት የሚገዙት፣ መኪና የሚገዙት፣ ድርጅት የሚከፍቱት፣ ልብስ የሚገዙት፣ ውጭ የሚሄዱት፣ ርዳታ የሚረዱት፣ ድግስ የሚደግሱት፣ ሞባይል የሚቀይሩት፣ ምክንያት ስላላቸው አይደለም፡፡ እገሌ ስላደረገው፣ የዘመኑ ፋሽን ስለሆነ፣ ሰው እጅ ላይ ስላዩት፣ የሆነ ሰው ሲያወራለት ስለሰሙ ብቻ ነው፡፡  

አንድ ሰው መንገድ ዳር ቆሞ ይለምናል፡፡ ‹‹አግኝቼ ያጣሁ ነኝ›› ይላል ደጋግሞ፡፡ ከሚያልፉት መንገደኞች አንዱ ጠጋ አለውና ‹‹እውነት አንተ አግኝተህ ያጣህ ነህ?›› ሲል ጠየቀው፡፡ ይለምን የነበረው ሰውም ‹አዎ›› ሲል መለሰ፡፡ መንገደኛውም ‹‹ለመሆኑ ከዶሮ ብልቶች በጣም ጣፋጩ ምንድን ነው?›› ሲል ጠየቀው፡፡ ሲለምን የነበረው ሰውም ‹‹ቆዳው›› ሲል መለሰለት፡፡ መንገደኛው ሰው ‹‹እውነትም አንተ አግኝተህ ያጣህ ነህ›› ብሎ ጠቀም ያለ ገንዘብ ሰጠው፡፡

ከጎኑ ቆሞ ሲያይ የነበረ አንድ ሰው ቀበል አደረገና ‹‹አግኝቼ ያጣሁ›› ማለት ጀመረ፡፡ 
ሌላ መንገደኛም ጠጋ ብሎ ‹‹አግኝተህ ያጣህ ከሆንክ ከበግ ሥጋ የሚጣፍጠው ምንድን ነው›› ሲል ጠየቀው

‹‹ቆዳ›› አለ አሉ፡፡

  © ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት የወጣ ነው

ኩራዝ ከጓሮ ማድቤት ተወሽቃ ትኖር ነበር፡፡ ለብዙ ዘመናት፡፡ ድንገት ሳሎን የምግብ ጠረጲዛ ላይ ታየች፡፡ ይህ ነገር ኮርኒስ ላይ የተንጠለጠለችውን አምፖል በእጅጉ አስገረማት፡፡

‹‹ኩራዝ፣ ዛሬ ከየት ከየት ተገኘሽ፡፡ እኔኮ እንደ ዳይኖሰር ዝርያሽ የጠፋ መስሎኝ ነበር›› አለች አምፖል እየተወዛወዘች፡፡

‹‹እናንተ የተጋደመ አታስተኙ፣ የተቀበረ አታስሞቱ›› አለቻት ኩራዝ ብል ብል እያለች፡፡ በዙሪያዋ የቤቱ ባለቤቶች ከብበው እራት ይበላሉ፡፡ ከተመጋቢዎቹ አንዱ ጭል ጭል በምትለው የኩራዟ ብርሃን በእንጀራው መሐል ያለውን ወጥ ፍለጋ ጠጋ ብሎ እያየ እንዲህ አለ፡-

‹‹ዛሬ ፌስ ቡክ ላይ ያየሁትን ግጥም ልንገራችሁ››

‹‹ምን ተባለ ደግሞ፡፡ ድሮ እረኛ ምን አለ? ነበር የሚባለው፡፡ ዛሬማ ፌስ ቡክ ምን አለ ሆነኮ፡፡›› አለችው የአባ ወራው ሚስት ወጡን ያገኘው ዘንድ ኩራዙን እያስጠጋችለት፡፡

‹‹እራትና መብራት ይባል ነበር ድሮ

እራቱም መብራቱም የት አለ ዘንድሮ›› አጨበጨበችለት፡፡ አምፖሏም ግርምቷን ይበልጥ በመወዛወዝ ገለጠችው፡፡ ኩራዝም ለመጎረር አስባ ትንሽ ኃይል ጨመረች፡፡ የሰውየውን ግጥም አጣጥማ ስትመለስም አምፖሏ ‹‹የጀመርሽውንኮ አልጨረስሽልኝም፡፡ የተጋደመ አታስተኙ፣ የተቀበረ አታስሞቱ ለምን አልሽን ›› አለቻት፡፡

‹‹እንዴ አዲስ አበባ ከተማ ላይ መብራት ከገባኮ መቶ ዓመት አለፈው፡፡ እኔ፣ ጧፍና ሻማ በቃን ብለን ጡረታ ወጥተን ነበር፡፡ ሻማና ጧፍም እንግዲህ ሲያረጁ ወደበተስኪያን ነው ብለው መንኩሰው በተስኪያን ገብተው ነበር፡፡ እኔም ባይሆን ስሜ እንኳን ለታሪክ ይቀመጥ ብል ስሜን ቀየራችሁት፡፡ ስሜ ከጠፋ እኔም ተረስቻለሁ ብዬ ሞቼ ነበር፡፡ እድሜ ለመብራት ኃይል እኔን ከተቀበርኩበት መቃብር፣ ሻማና ጧፍን ከመነኮሱበት ገዳም አመጣን፡፡ መቼም እናንተ ያለውን ከማክበር ይልቅ የሞተውን መቀስቀስ ትወዳላችሁ፡፡ ቆይ ግን አንቺና ፍሬቻ ልዩነታችሁ ምንድን ነው?››

‹‹ምን ልዩነት አለን፡፡ እርሱ መኪና ላይ እኔ ኮርኒስ ላይ ከመሆናችን በቀር፡፡ ያው ሁለታችንም ቦግ እልም ነው የምንለው፡፡ ሳንጠፋ ማብራት አይሆንልንም፡፡ ድሮ እኔ ሳቀው ቦግ እልም ብልጭ ድርግም የሚሉ ሦስት ነገሮች ብቻ ነበሩ››

‹‹ምን ምን ናቸው?››

‹‹አንድ መብረቅና፤ ከነ ድምጡ ብልጭ ብሎ ድርግም ይላል፡፡ ሁለት የገና መብራት፣ የገና ዛፍ ላይ ተጠብልሎ ቦግ እልም ይላል፡፡ ሦስት የዳንስ ቤት መብራት፣ ከሙዚቃ ጋር ተዋሕዶ በሙዚቃው ድምጥ ቦግ እልም ይላል፡፡ አሁን አሁንማ ወይ እንደ መብረቅ ነጎድጓድ የለኝ፣ ወይ እንደ ገና መብራት ዛፍ ላይ አልተንጠለጠልኩ፣ ወይ እንደ ዳንስ ቤት ሙዚቃ የለኝ እንዴው ብቻዬን ቦግ እልም ስል አመሻለሁ፡፡ አገልግሎቴኮ የሰዓት መቁጠሪያ ሆነ፡፡ መጀመሪያ መብራት የጠፋ ጊዜ፣ ሁለተኛ የጠፋ ጊዜ እየተባለ ሰዓት ይቆጠርብኛል፡፡ እንዴው ግን በናንተ ዘመን ሄደ መጣየሚባል ነገር ነበር እንዴ?››

‹‹ነበረ እንጂ›› አለች ኩራዝ፡፡ ‹‹ነጋዴ ሄደ መጣ፣ ወታደር ሄደ መጣ፣ እድሜ ሄደ፣ መሬት ሄደ መጣ፡፡ ስንት የሄደና የመጣ ነገር አለ፡፡››

‹‹መብራትስ ይሄድ ነበር››

‹‹መብራት መጣ፣ መብራት ሄደ አሁን እናንተ ስትሉ ነው የምሰማው፡፡ የመሠረተ ትምህርት ማስተማሪያ ላይ እንኳን አበበ ሄደ፣ ከበደ መጣ የሚል እንጂ መብራት ሄደ መብራት መጣ የሚል አላየሁም፡፡ እኛኮ በቅብዐ ኑግም ብትይ፣ በጥጥ ዘይትም ብትይ፣ በጉሎ ዘይትም ብትይ እንሠራ ነበር፡፡ ከባሰ ደግሞ ጤፍ የምታስለቅም ጨረቃ ትወጣለች፡፡ ያለበለዚያ ምድጃ ከብበሽ እሳት ዳር መብላት መጠጣት ነው፡፡ የእናንተኮ የሚገርም ነው፡፡ ዘይት መሥራቱን ኋላ ቀርነት ብላችሁ ተዋችሁት፡፡ ምድጃ ዳር እንዳትቀመጡ ሳሎናችን ለቴሌቭዥንና ለሶፋ ብቻ ነው አላችሁ፡፡ ከሁለቱም ያጣችሁ ሆናችሁኮ፡፡ እንደ ዘንድሮ ነጋዴኮ መከራ ያየ የለም፡፡ ገቢዎች፣ ጉምሩክ፣ ንግድ ቢሮ፣ ቀበሌ፣ ክፍለ ከተማ ማስታወቂያ ያወጣሉ፡፡ በቴሌቭዥንና በሬዲዮ ያስነግራሉ፡፡ ገና ማስታወቂያው ሲጀምር መብራቱ እልም፡፡ ተመዝገቡ ይባል፣ ክፈሉ ይባል፣ ተሰለፉ ይባል፣ ወረፋ ያዙ ይባል፣ ጥፉ ይባል፣ ሽሹ ይባል በምን ይታወቃል፡፡ ከዚያ ትቀጫለሽ ትባያለሽ›› ‹‹ምነው›› ያልሽ እንደሆነ ማስታወቂያ በቴሌቭዥንና በሬዲዮ ነግረን ነበር ይሉሻል፡፡ እነርሱ መናገራቸውን እንጂ እኛ አለመስማታችንን አያዩ፡፡ ቴሌቭዥንና ሬዲዮኮ ለራሳቸው እንጂ ለሁላችን የሚሆን ጀነሬተር የላቸውም፡፡ የስንቱ ሞያ ተበላሸ በእናንተ ምክንያት፡፡ ግማሽ በስሎ ግማሽ ሳይበስል የሚወጣ እንጀራ ምን እንደሚባል ታውቂያለሽ?››

አምፖል መልሱን ለመስማት ጓጉታ ‹‹አላውቅም›› አለች

‹‹የመብራት ኃይል እንጀራ›› ይባላል፡፡

አምፖል በሳቅ ስትፈርስ በውስጧ የነበሩት ቀጫጭን ሽቦዎች ረገፉ፡፡ ደነገጠች፡፡

‹‹አንቺ ሳልቃጠል አልቀርም›› አለቻት ኩራዝን፡፡

‹‹ምን የተቃጠለውም ያልተቃጠለውም አምፖል አንድ ነው፡፡ ሁለታችሁም አትበሩም፡፡ አይዞሽ ማንም አያውቅሽም፡፡ እዚህ ሀገር እንደሆነ የሚሠራው ከማይሠራው ጋር አብሮ ነው የሚኖረው››

‹‹እንዴት እንዴት››

‹‹ለምሳሌ መብራት ኃይል ሲባል ሰምተሻል? ኃይል አለ መብራት የለም፡፡ ኔት ወርክ ሲባል ሰምተሻል? ‹ኔት› አለ ‹ወርክ› ግን የለም፡፡ ቴሌ ኮሙኒኬሽን ሲባል ሰምተሻል? ‹ቴሌ› አለ ‹ኮሙኒኬሽን› ግን የለም፡፡ የሃይማኖት ተቋም ሲባል ሰምተሻል? ‹ሃይማኖት› አለ ‹ተቋም› ግን የለም፡፡ ስፖርት ፌዴሬሽኖችን አልሰማሽም? ‹ስፖርት› የለም ‹ፌዴሬሽን› ግን አለ፡፡ የደንበኛ አገልግሎት ሲባልስ? ‹ደንበኛ› አለ፤ ‹አገልግሎት› ግን የለም፡፡ ነጻ ፕሬስ ሲባልስ? ‹ፕሬስ› አለ ‹ነጻ› ግን የለም፡፡ የርዳታ ድርጅት ሲባልስ? ‹ድርጅት› አለ ‹ርዳታ› ግን የለም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሲባሉስ አልሰማሽም? ‹ፓርቲ› አለ ‹ፖለቲካ› ግን የለም፡፡ ነጻ ገበያስ አታውቂም? ‹ገበያ› አለ ‹ነጻ› ግን የለም፡፡ ዴሞክራሲ ሲባልስ አልሰማሽም? ‹ዴሞ(ሕዝብ)› አለ፣‹ክራሲ(አስተዳደር)› ግን የለም፡፡ በየቢሮው በኮምፒውተር ሲስተም መሥራት ጀምረናል ሲሉ አትሰሚም አዎ ኮምፒውተር በየቢሮው አለ ‹ሲስተም›› ግን የለም፡፡ እንዲህ እያልሽ መቀጠል ነው፡፡››

‹‹ መቃጠሌን ያወቁብኝ እንደሆነ ግን ከዚህ ቦታ መውረዴ ነው››

‹‹ተይ እባክሽ እዚህ ሀገር አንቺ ብቻ ነሽ እንዴ ስትቃጠይ የምትወርጅው፡፡ በየመሥሪያ ቤቱ፣ በየፓርቲው፣ በየእምነት ተቋሙ፣ በየግል ድርጅቱ ስንት የተቃጠለ አምፖል አለ አይደለም እንዴ፡፡ ማን አወረደው፡፡ መብራት ስለሌለ ማንም ሳይለየው የሚሠራ  አምፖል መስሎ ይኖራል፡፡ አየሽ ጨለማ ለአጭበርባሪ ይመቻል፡፡ በብርሃን ግን ሁሉ ይገለጣል፡፡ እንዲህ ጨለማ የምንሆነው ኤሌክትሪክ በሀገር ጠፍቶ መሰለሽ?››

‹‹ታድያ ለምንድን ነው?››

‹‹ብርሃን ለማጭበርበር ስለማያመች ነው፡፡ ብርሃን ከመጣ የሚወልቁ ብዙ የተቃጠሉ አምፖሎች አሉ፡፡ ተቃጥሎ ቦታን ላለመልቀቅ ዋናው መፍትሔ ጨለማ ነው፡፡›› ኩራዝ ይህንን ስትል የቤቱ አባወራ መጣና ‹እፍ› ብሎ አጠፋት፡፡

‹‹በይ ደኅ እደሪ፣ እፍ ብለው ያበሩናል እፍ ብለው ያጠፉናል›› አለችና ቆርቆሮዋ ውስጥ ገብታ ተኛች፡፡  

© ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ የወጣ ነው

ቀነኒሳን አንበሳ አሉት፡፡ ኃይሌንም አንበሳ አሉት፡፡ እንደምን ነው ቢሉ፡፡ አንድም አንበሳ ሲተኛ የሞተ፤ የደከመ፣ የታመመ ይመስላል፡፡ እንስሳት እየመጡ ይጎበኙታል፡፡ ያዩታል፤ አንዳንዶቹም ይራመዱታል፡፡ ሌሎቹም አንበሳው ደክሟል ብለው የአራዊት ንጉሥ እኛ ነን ይላሉ፡፡ እንደ ዝንብ ያሉትም ይወርሩታል ‹‹አንበሳ ሲያረጅ የዝንብ መጨዋቻ ይሆናል›› እንዲሉ፡፡ እርሱ ግን የሚያደርገውን ያውቃልና ዝም ይላቸዋል፡፡

ታሪክ እንደ አንድ አንበሳና አይጥ፡፡ ታሪኩስ እንደምን ነው ቢሉ እንዲህ ነው፡፡ በአንድ ጫካ የሚኖር አንበሳ ደከመውና አፉን ከፍቶ ተኛ፡፡ እንደተኛም አንዲት አይጥ መጣች፤ መጥታም አልቀረች ትዞረው ጀመር፡፡ ወደ ወገኖቿም ሄዳ አንበሳ ደክሞ ተኝቷል ብላ በሰፊው አወራች፡፡ ተመልሳም መጣችና ተጠጋችው፡፡ እርሱም ዝም አላት፡፡ እርሷም ጠጋ ብላ ጅራቷን በአፍንጫው ከተተችበት፡፡ እንዳያነጥስ ችሎ ዝም አላት፡፡ አይጧም ጠጋ ብላ አፉን ተመለከተችው፡፡ ምቹ ዋሻ መስሎም ታያት፡፡ አሁንም ተጠጋች፡፡ በመጨረሻም ያንን የተከፈተ ዋሻ ልትጎበኝ ወደ አፉ ውስጥ ዘው አለች፡፡ ያን ጊዜም አንበሳ አፉን ግጥም አደረገው፡፡ ሲጥ ብትል ሚጥ መውጫ አልተገኘም፡፡

ቀነኒሳም እንዲሁ ነው፡፡ እርሱ ከውድድር ሲርቅ ደከመ፣ ሰለቸ፣ መከነ፣ ተወ፤ ተብሎ ነበር፡፡ ሌሎችም እኛ የትራክ ላይ ንጉሦች ነን፡፡ የጎዳና ላይ ነገሥታት ነን ብለውም ነበር፡፡ እንደ አይጧም ብዙ ወሬ አውርተው ነበር፡፡ አፈፍ ብሎ ሲነሣ ግን እነዚያን ሁሉ ድል ያደርጋቸዋልና ቀነኒሳን አንበሳ ብለውታል፡፡


አንድም አንዱ አንበሳ ሲያድን ሌላው አንበሳ በሦስት ነገር ይረዳዋል፡፡ አንድም አካባቢውን በመጠበቅ፣ አንድም ታዳኙን በማድከም፣ አንድም አዳኙን በማጀብ፡፡ ኃይሌም እንዲሁ ነው፡፡ ቀነኒሳን በለንደኑ ሩጫ በሦስት ነገር ረድቶታል፡፡ አንድም የሩጫውን ሂደትና ድል በመጠበቅ፣ አንድም ሞ ፋራህን በማድከም፣ አንድም ቀነኒሳን በማጀብ፡፡ አንበሳ ሲያጠቃ በቡድን ነው፡፡ ኃይሌና ቀነኒሳም በቡድን አጥቅተዋልና አንበሶች ተብለዋል፡፡ ኃይሌ ከቀናት በፊት ስለ ሞ ፋራህ የሰጠው አስተያየትና ለቀነኒሳ የሰጠው ምክር ለለንደኑ የቀነኒሳ ድል ረድቶታልና ኃይሌን አንበሳ ብለውታል፡፡

አንድም ኃይሌን በስፖርተኛ የዕርግን ዘመኑ ባስመዘገበው ውጤት አንበሳ ብለውታል፡፡ እንደምን ነው ቢሉ፡፡ አንበሳ ቢያረጅም እንኳን ፈጽሞ ካልወደቀ በቀር እንስሳት አይተው ይፈሩታል፡፡ እርሱም ተንቀሳቅሶ በዐቅሙ ያድናቸዋል፡፡ ኃይሌም ምንም በዕድሜ ቢገፋ ሯጮች አይተው ይፈሩታል፡፡ ሮጦም ድልን በዐቅሙ ያድናልና አንበሳ ብለውታል፡፡

ነገር እንደ ተረትና ምሳሌ

አንበሳ ተኝቶ ፍየል ዘለለችው

ንቆ ቢያሳልፋት ሞኝ አደረገችው

አንድም አንበሳ በሦስት ነገር ተፈርቶ ይኖራል፡፡ አንድ በድምጹ፣ ሁለት በግርማ ሞገሱ፣ ሦስት በክርኑ፡፡ በድምጹ እንደምን ነው ቢሉ አንበሳ ገና ከሩቁ ሆኖ ሲጮኽ ሲሰሙት እንስሳቱ ሁሉ ይርዳሉ፣ ይንቀጠቀጣሉ፡፡ በግርማ ሞገሱስ እንዴት ነው ብለው ቢጠይቁ አንበሳ ባይጮኽም ባይባላም በጫካው ውስጥ ጎምለል ጎምለል ሲል እንስሳቱ ፈርተው ይሸበራሉ፡፡ በክርኑስ እንደምን ነው ያሉ እንደሆን በእግሩ ርግጥ አድርጎ በክርኑ አድቅቆ ይመገባልና ነው፡፡ ቀነኒሳም አንበሳ ነው ሲሉ ምንም ባያሸንፍ እንኳን እዚህ ውድድር ላይ ሊወዳደር ነው፣ ሊሮጥ ነው ሲባል አብረውት የሚሮጡ ሁሉ ይፈራሉ ይርዳሉ፡፡ አንድም ምንም ባያሸንፍ እንኳን እርሱ በውድድሩ ውስጥ ገብቶ ሲሮጥ ሲያዩት ድል ይነሣን ይሆናል ብለው ብዙዎቹ ሯጮች ይሸበራሉ፡፡ አንድም አምርሮ የሮጠ እንደሆነ ደግሞ ኃያላኑን ከኋላው አስከትሎ ድል በኃያል ክንዱ ድል ያደርጋቸዋልና ነው፡፡

አንድም አንበሳ ከአፍሪካ ሄዶ በእንስሳት ማቆያ ውስጥ ካልሆነ በቀር በፈረንጅ አገር አይገኝም፡፡ እንደ ቀነኒሳ ያለ ሯጭም ከአፍሪካ ሄዶ ለሰው ሀገር ይሮጥ ይሆናል እንጂ በፈረንጅ አገር አይገኝምና ቀነኒሳን አንበሳ ብለውታል፡፡ አንድም አንበሳ የሀገራችን የጀግንነት፣ የአልበገር ባይነትና የድል አድራጊነት ምልክቷ ነው፡፡ ኃይሌና ቀነኒሳም በረሃብ፣ በችግርና በጦርነት ስሟ በክፉ የሚነሣውን ሀገራችንን በጀግንነት፣ በድል አድራጊነትና በአልበገር ባይነት እንድትታወቅ አድርገዋታልና አንበሳ ተብለዋል፡፡

ያሉንን አናብስት እያወደስን ሌሎች አናብስትን እናፈራለን፡፡ 

እዚያው ፉትስክሬይ ቁጭ ብለን ወግ በመሰለቅ ላይ ነን፡፡ ባለፈው ወዳጄ ስለ ‹‹ኢምፖርት›› አንሥቶ ነበር ያቆመው፡፡ እስኪ ይቀጥል፡፡
‹‹ምንድን ነው ኢምፖርት የሚያደርጉት ኢትዮጵያ ሄደው››

‹‹ሚስት ነዋ››

‹‹እንዴት ነው ደግሞ ሚስት ኢምፖርት ማድረግ ማለት››

‹‹እዚህ ሀገር ያለ ሐበሻ በሦስት መንገድ ነው ሚስት የሚያገኘው››

‹‹በምን በምን››

‹‹በኢምፖርት፣ በኤክስፖርትና በባላንስ››

‹‹ይሄ ትርጓሜ ያስፈልገዋል››

‹‹ኦኬ፤ ኢምፖርት የሚባለው ሀገር ቤት ትሄድና ሚስት ወይም ባል ይዘህ ስትመጣ ነው፡፡ ኤክስፖርት የሚባለው ደግሞ የውጭ ሀገር ሰው በተለይም የዚህን ሀገር ሰዎች ስታገባ ነው፡፤ ባላንስ ሠራህ የሚባለው ደግሞ ሁለት አበሾች እዚሁ ተገናኝተው ሲጋቡ ነው፡፡››

‹‹ታድያ የትኛው ነው የሚሻለው››

‹‹ሁሉም የራሱ ጣጣ አለው፡፡ ኢምፖርት ስታደርግ ከታደልክ ትዳር የጠማትን ወይም የጠማውን ታገኘዋለህ ወይም ታገኛታለህ፡፡ ካልታደልክ ደግሞ እዚህ ከመጣች በኋላ አቢዩዝ አደረገኝ ብላ ልትፈነግልህ ትችላለች፡፡ ወንዱም ትቷት ሊሄድ ይችላል፡፡ ወይም ይፋታሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እዚህ ኢምፖርት ተደርገው ከመጡ በኋላ ስቃያቸውን ያዩም አሉ፡፡ ውጭ እንሄዳለን፣ ባል እናገኛለን፣ አለፈልን ብለው ሳያመዛዝኑ ውጭ ሀገር ስለተባለ ብቻ ይመጡና አበሳቸውን ያያሉ፡፡ በተለይ ስደት ላይ ብዙ ዘመን ኖረው፣ እድሜያቸውን ጨርሰው፣ ራሳቸውን መልጠው፣ ሁለት ጠጉር አውጥተው ከሀገር ቤት ዘልላ ያልጨረሰች ሚስት የሚያመጡ ፌንት ይገጫሉ፡፡››

እንዴት ነው የሚገጩት››

‹‹አየህ አንተ ሃያ ዓመቷን ሱዳንና ኬንያ ከጫርካት በኋላ አባባ የምትልህን ቆንጆ ልጅ ስታመጣ፤ እርሷ እያማረባት ሲሄድ አንተ ግን እድሜ ሲያናጭርብህ ቅናቱን አትችለውም፡፡ የነገር አባቷ እንጂ ባሏ ስለማትመስል ሥጋት እየገባህ ይሄዳል፡፡  ያም ያም አንተን ረስቶ የሚስትህን ቁንጅና ሲያወራ እርሷ ተጨዋች አንተ ተመልካች የሆንክ ይመስልሃል፡፡ ያን ጊዜ አበሻነትህ ይነሣብሃል፡፡ አውስትራልያ መሆንክን ትጠላውና መንዝና ሞላሌ፣ ወልቃይት ጠገዴ፣ ሽሬ እንዳ ሥላሴ መሆን ያምርሃል፡፡ መሳደብ፣ መጨቃጨቅ፣ ሲብስም መማታት፣ ሲያልፍም አካል መጉዳት፣ በመጨረሻም ሕይወት እስከ ማጥፋት ትሄዳለህ፡፡

እዚህ ሜልበርንኮ አንዱ እልኩና ቅናቱ አልወጣለት ሲል ከሕንድ ቤት ቀይ ቃርያ ገዝቶ ሚስቱን በበርበሬ አጥኗታል፡፡ ስንቱ ሚስቱን ገድሏል፤ ስንቶቹስ ተደብድበውና ተፈንክተው በሐኪም ጥረት ከሞት ተርፈዋል፡፡ ኢምፖርት ዕዳው ብዙ ነው፡፡

የዚህን ሀገር ሰዎች አግብተው የሚኖሩ ብዙ አበሾች አሉ፡፡ በተለይ ሴቶቹ በዚህ ጎበዞች ናቸው፡፡ እነርሱ ጋር እስካሁን የሰማሁት የከፋ ችግር የለም፡፡ ባይሆን ወንዶቹ ፈተና ይገጥማቸዋል፡፡ ፈረንጅ ወዳጄ ፍቅራዊ (ሮማንቲክ) ነገር ይወዳል፡፡ እኛ ደግሞ ሃኒ፣ ስዊት፣ ዳርሊንግ የሚል ነገር አልለመድነው፡፡ እኔ ሐኒ የማውቀው ከሦስተኛ ክፍል ጀምሮ ማር በእንግሊዝኛ ሐኒ መሆኑን ነው፡፡ ስዊት – ጣፋጭ ነው፤ በቃ፡፡ ዳርሊንግ እዚህ ነው የሰማሁት፡፡ እኛ ደግሞ ቆፍጠን ያልን ነን፡፡ ‹ሌቱን ለአራዊት ቀኑን ለሠራዊት› ነው ወዳጄ፡፡ የኛ አኗኗር ለእነርሱ መሥሪያ ቤት ይሆንባቸዋል፡፡ እንኳን እነርሱ እዚህ ሀገር ቆየት ያሉት ሴቶች እንኳን ‹‹የኛ ወንዶች አባወራነት እንጂ ፍቅረኛነት አይችሉም›› ይሉናል፡፡

ከቻልክ እዚህ ሀገር ባላንስ መሥራት ነው፡፡ ተዋውቀህ፣ ሀገሩንም ዐውቀህ መጋባት፡፡ ችግሩ እዚህ እንደ አሜሪካ ዲቪ የለ፣ እንደ አውሮፓ በመርከብ የሚገባ የለ፣ ከየት ታመጣለህ፡፡ ወይ እዚያው ስደት ላይ ተጋብተህ ካልመጣህ በቀር፡፡ ››

‹‹ይህን ችግርኮ ተባብራችሁ መፍታት ትችሉ ነበር››

‹‹አንዳንዱን አበሻ ተባበር ከምትለው ተሰባበር ብትለው ይሻለዋል፡፡ ሁሉም በየጎጡና በየሠፈሩ ነው፡፡ አብዛኞቹ ቤተ ክርስቲያኖች እንኳን ዘርን መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ የአማራውን፣ የትግሬውን፣ የኦሮሞውን ቤተ ክርስቲያን ትለየዋለህ፡፡ ትግሬውም አንድ መሆን እያቃተው አድዋ፣ ሽሬ ሲል ታገኘዋለህ፡፡ አማራውም ወልቃይት፣ ጎንደር እየተባባለ ለብቻው ቸርች ይከፍትልሃል፡፡ ኮሙኒቲውም ለየብቻ ነው፡፡ እዚህ ሀገር የኦሮሞ፣ የሶማሌ፣ የሐረሪ፣ የትግራይ ኮሙኒቲዎች አሉ፡፡ አንደኛው ከአንደኛው ጋር የሚጠራጠሩ፣ የማይተባበሩ፡፡ ከትብብር ርቀው ንጽሕ ጠብቀው የሚኖሩ፡፡ በፍቅር የተጎዱ፣ ከኅብረት የጸዱ፡፡ አንዳንዶቹ ኢትዮጵያውያን ነን ይላሉ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ‹‹ምሥራቅ አፍሪካ›› የሚባል ሀገር ፈጥረውልሃል፡፡ …››

‹‹ኧረ እንዲያውም አዳሙ ተፈራ በጻፈው ‹‹ገመናችን በሰው ሀገር› የሚለው መጽሐፍ ላይ ሜልበርን የሚገኘው የኦሮሞ ኮሙኒቲ በ2010 እኤአ 25ኛ ዓመቱን ሲያከብር የጻፈውን አይቼ ገርሞኝ ነበር፡፡

‹‹The Oromo are indigenous African people from the north eastern of Africa.›› ይላል፡፤ ኢትዮጵያ ላለማለት አዲስ ሀገር ፈጥረዋል፡፡ ››

‹‹እይውልህ እንደዚያ ነው እንግዲህ፡፡ የሚገርምህኮ እዚህ ያለ ሰው መገንጠልን የሚጠላ ተገንጣይ መሆኑ ነው››

‹‹በዚህ ብቻ አይበቃም ትርጓሜ ያሻዋል – ብሏል ኪነ ጥበብ›› አልኩት፡፡

‹‹በውጭ ያለ ዳያስጶራ ስለ ኤርትራ መገንጠል ሁል ጊዜ እየተንገበገበ ያወራል፡፡ እርሱ ግን ራሱ በፈቃዱ ያለ ሪፈረንደም ተገነጣጥሏል፡፡ በምትቃወመው ነገር ውስጥ ራስህን እንደማግኘት ያለ አስነዋሪ አካሄድ የለም፡፡ በየስብሰባው ‹ዐንቀጽ 39› የምትባል ነገር ትነሣለች፡፡ ‹‹የብሔረሰቦች መብት እስከ መገንጠል›› የምትባለው፡፤ ይህች ዐንቀጽ እስካሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ አልተደረገችም፡፡ እዚህ ግን ተግባራዊ ተደርጋለች፡፡ የተገበሯት ደግሞ የሚቃወሟት ሰዎች ናቸው፡፡ ለዚህ ነው ‹‹መገንጠልን የማይደግፍ ተገንጣይ›› ያልኩህ፡፡ አሁን ዘመን መለወጫ እየመጣ አይደለ? ሦስት ቦታ ነው ፕሮግራም የተዘጋጀው፡፡ ከዚያ መርጠህ እንደየብሔረሰብህ መሄድ ነው፡፡ ወዳጄ እዚህ ሀገር ጩኒ ይምጣብኝ››

‹‹ማነው ጩኒ ደግሞ››

‹‹ጩኒ ሰው አይደለም፤ ሕዝብ ነው››

‹‹ጩኒ የሚባል ሕዝብ፤ ለመጀመሪያ ጊዜ መስማቴ ነው፡፡››

‹‹ጩኒ ማለት ቻይና ነው፡፡ እዚህ ሀገር ጩኒ ነው የምንላቸው፡፡ ጩኒ እርስ በርስ በመደጋገፍ ማንም አይችላቸውም፡፡ ብድር ይሰጡሃል፤ መረጃ ይሰጡሃል፡፡ ያቋቁሙሃል፡፡ ከዚያ ምርጥ ኢንቨስተር ትሆናለህ፡፡ ያለበለዚያ ደግሞ ወጥሬ እሠራለሁ ካልክ በቀላሉ የምትከራየው ቤት ይሰጡሃል፡፡ እንዲት ክፍል ተከራይተህ ኑሮ ሳይከብድህ ወጥረህ ትሠራና በዓመትህ ቀና ትላለህ፡፡ ወዳጄ ጩኒ አንገቱን ደፍቶ እየሠራ ልጁን ምርጥ ትምህርት ቤት ነው የሚልከው፡፡ ኮሙኒቲያቸው ልጆቹን በሚገባ ነው የሚረዳቸው፡፡ ስለዚህ ልጆቹ ውጤታማ ናቸው፡፡ እኛጋኮ ወላጆችና ልጆች አልጣጣም ብለዋል፡፡ ልጆቹን የቤት ሥራ ማን ያሳያቸው፡፡ ማን በትምህርት ያግዛቸው፡፡

አገርሽ ምንኛ መንደርሽ ምንኛ

አላውቅበት አልኩኝ ያንችን አማርኛ

ሲባል አልሰማህም፡፡ በምን ቋንቋ በምን ዕውቀት ከልጆቻችን ጋር እንግባባ፡፡ ልጆቻችን አያውቁም ብለው ንቀውናል፡፡ በዚህ የተነሣ ከትምህርት የሚያቋርጡት ብዙ ናቸው፡፡››

‹‹ቆይ ግን እዚህ መጥተው የተሳካላቸው የሉም››

‹‹ለዓይነት ያህልማ አሉ፡፡ መቼም ለስማችን መጠሪያ ቁና ሰፍተናል፡፡ ለአካባቢ ምርጫ እስከመወዳደር የደረሱ አሉ፡፡ ያው ከሆቴልና እንጀራ ቤት ባናልፍም ቢዝነስ ያላቸውም አሉ፡፡ በተማሩት ሞያ የሚሠሩም በመጠኑ አሉ፡፡ እኔ የሚገርመኝ ግን በኢሕአፓ፣ በኢሕአዴግ፣ በግንቦት ሰባት፣ በኢዲዩ፣ በቅንጅት ውስጥ ለመግባት እንጂ በምንኖርበት ሀገር በሚገኙ ፓርቲዎች ውስጥ ገብቶ፣ አባል ሆኖ፣ ተወዳድሮ ፓርላማ ለመግባት፣ የአካባቢ ተመራጭ ለመሆን የሚተጋ አበሻ ብዙ አናይም፡፡ አሜሪካ እንኳን ሚሊዮን የሚሞላ ኢትዮጵያዊ ተከማችቶ እስካሁን አንድ የአካባቢ ተወካይ እንኳን አለማግኘታቸው ይገርመኛል፡፡ እኛ በሀገራችን አምባሻ ነው የምንራኮተው፡፡ ለምሳሌ እዚህ አውስትራልያዊ ዜግነት ካለህ መምረጥ ግዴታህ ነው፡፡ እንደ አሜሪካ አይደለም፡፡ የመምረጥ ግዴታ አለብህ፡፡ ያለበለዚያ ቅጣት አለው፡፡ የፓርቲዎቹ አባል ስትሆንና ሳትሆን ዕድልህ ይለያያል፡፡ if you are not a member, you are a number ይሉሃል፡፡ ችግሩ ግን እዚህ ሀገር ተመልካች እንጂ ተጨዋች የለም፡››

‹‹ማለት››

‹‹ኳሱ ጉዳያችን ነው፡፡ ሜዳው አውስትራልያ ይባላል፡፡ ሕጉ የሀገሪቱ ሕግ ነው፡፡ ዳኛው ሲስተሙ ነው፡፡ ዋንጫው ውጤትህ ነው፡፡ እዚህ በሚገባ ተጫውተህ የስኬትን ዋንጫ መሳም ትችላለህ፡፡ ምን ያደርጋል ታድያ፡፡ በዙሪያህ ቆሞ ለምን ይህ አይሆንም? ለምን ይሄ አይደረግም? እገሌ ለምን እንዲህ ያደርጋል? እንዲህ በመሆኑ አኩርፌ ቀርቻለሁ፣ የሚል የዳር ተመልካች እንጂ ሜዳው ውስጥ ገብቶ ለመጫወት የሚፈልግ የለም፡፡ እዚህ ያለውን ሰው ‹‹ሰይጣን›› ከምትለው ‹ኮሙኒቲ› ብትለው ደንግጦ ያማትብብሃል፡፡ ተበላ፣ ተጠጣ፣ ተጣሉ፣ ተከፋፈሉ ብቻ ነው የምትሰማው፡፡ አንድ ወዳጄ ምን ይላል መሰለህ

የትልቅ ሰው ልጅ ቀረ በከንቱ

ሀገር ሳይገዛ ሳይባል አንቱ – እንዲህ ነው እንግዲህ፡፡

ካሮላይን ስፕሪንግስ፣ አውስትራልያ

በአበሾቹ መንደር ፉት ስክሬይ በአንዱ የሐበሻ ሆቴል ቁጭ ብዬ አንድ ወገን ወደ እኔ መጣ፡፡ መጥቶም አልቀረ ወንበር ሳበና ቁጭ አለ፡፡

‹‹ዐውቅሃለሁ መሰል››

‹‹ይሆናል፣ የሰው መተዋወቂያው ብዙ ነው›› አልኩት፡፡

‹‹ዳንኤል ነህ አይደል›› አለኝ፡፡ አረጋገጥኩለት፡፡ እኔ በቀን አራት ጊዜ የሚፈራረቀው የሜልበርን አየር አልገባኝ ብሏል እርሱ ጃቦኒ ነው ያደረገው፡፡ ራሱን አስተዋወቀኝ፡፡ መጽሐፎቼን ማንበቡን ነገረኝ፡፡ መቼም በውጭ ሀገር ሰማሁ የሚል እንጂ አየሁ፣ እገሌ ነገረኝ የሚል እንጂ አነበብኩ የሚል ሰው ማግኘት ዋድላና ደላንታ ሄዶ ኦራል እንደማግኘት ብርቅ ነው፡፡ አመሰገንኩት፡፡

‹‹እንግሊዝኛ ብችል ኖሮ አንዳንዱን ጽሑፍ እተረጉመው ነበር›› አለኝ እየሳቀ፡፡

‹‹ታድያ ምን ችግር አለው፡፡ አውስትራልያ የእንግሊዝኛ ሀገር ናት፡፡ ተርጉመው›› አልኩት፡፡

‹‹እንደመጣሁ ቋንቋ ትምህርት ቤት ገብቼ ነበር፡፡ ለስደተኞች የሚሰጥ ኮርስ ስላለ ለመውሰድ፡፡ እንግሊዝኛና ብስክሌት በልጅነት ካልጀመሩት ጉድ ይሠራል››

ሳቅኩና ‹‹እንዴት?›› አልኩት››

‹‹ሞከርኩትና ቋንቋውን ትቼ ፈገግታውን ብቻ ተምሬው ወጣሁ›› አለኝ፡፡

‹‹የትኛውን ፈገግታ?››

‹‹አለች የእነርሱ ፈገግታ፤ እንደ ፍሬቻ ብልጭ ድርግም የሚያደርጓት፡፡ ቢገባህም ባይገባህም ከሳቅክ ፈረንጅ ደስ ይለዋል፡፡ ታድያ ሥራ ስገባ ቢገባኝም ባይገባኝም ሳቅ ስል ከአፍንጫ በታች ከአገጭ በላይ በሆነ ፈገግታ ያጅቡኝ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ ሥራዬን ከሠራሁ የእነርሱ እንግሊዝኛ ቢገባኝ ባይገባኝ ብዬ ተውኩላቸው፡፡ አንድ ቀን ግን ጉድ ሆንኩ፡፡›› ጉጉቴ ከሳቅ ጋር ጨመረ፡፡

‹‹አንድ አብሮኝ የሚሠራ ልጅ አለ፡፡ በጉሮሮ እንግሊዝኛው ሲያወራኝ ስቄ ነበር የማሳልፈው፡፡ ‹እንግሊዝኛንና ስደትን ስቆ ማሳለፍ ነው› የሚል ጓደኛ ነበረኝ፡፡ ታድያ አንድ ቀን ሥራ እየሠራን የሆነ ነገር ያወራኛል፡፡ ልብ አልሰጠሁትም፡፡ ሲጨርስ ቀና ብዬ በፈገግታ ሳየው ተናደደ፡፡ በማውቃት እንግሊዝኛ ‹‹ምን ሆንክ›› አልኩት፡፡ ‹‹እንዴት እናቴ ትናንት ሞተች ስልህ ትስቃለህ›› አይለኝም፡፡ እኔ ራሴ ደነገጥኩ፡፡ ቀዥቃዣ ፈረንጅ፤ እናቱ ሞታ እስኪ ከፍራሽ አስነሥቶ ሠለስት እንኳን ሳይደርስ ምን ያመጣዋል፡፡ እኛ ድሮ የተማርነውን ሁሉ አጣመው አጣመው ድምጻቸው ሊያዝልኝ አልቻለም፡፡ አሁን ሲገባኝ ግን እነርሱ የጉሮሮ እኛ የከንፈር እንግሊዝኛ ነው የተማርነው፡፡››

‹‹ደግሞ እንግሊዝኛ የከንፈርና የጉሮሮ የሚባል አለው?››

‹‹ታድያስ፡፡ እስኪ ስማቸው፡፡ እኛ ‹ዋተር› ብለን ረገጥ አድርገን ስንጠራ እነርሱ ‹ዋር› ብለው በአየር ላይ ያልፉታል፡፡ እኛ ‹ገርል› እየተባልን ጫን ብለን ስንናገር እነርሱ ‹ገ – ል› ብለው በስሱ ያቆላምጧታል፡፡› አሁን ያለን አማራጭ በአማርኛ እያለቀስን በእንግሊዝኛ መሳቅ ነው፡፡›› እኔ ግን በአማርኛ ሳቅኩ፡፡

‹‹ለምን ትምህርት ቤት አልሄድክም(ውጭ ‹አልገባህም› አይባልም) እዚያ የግድ ከቋንቋው ተናጋሪዎች ጋር ስትቀላቀል ትለምደው ነበር››

‹‹ድመት ጅራቷ የተቆረጠበት ቦታ ተመልሳ አትሄድም› ሲባል ሰምተሃል፡፡ እኛም መቀመጫችንን (እርሱ ሌላ ነበር ያለው) የተገረፍንበት ስለሆነ ነው መሰል ወጣ ስትል እዚያ አይመራህም፡፡ እንጂ እዚህ ሀገርማ ብትማር ብዙ ይረዱሃል፡፡ አየህ ድሮ እንማር የነበረው ለእንጀራ ነበር፡፡ እዚህ መጥተን ሳንማር እንጀራ አገኘን፡፡ ታድያ ለምን እንማራለን? ደግሞ በየስደተኛው ካምፕ ፀጉራችንንና ልባችንን ጨርሰን መጥተን ነው መሰል እዚህ ሀገር ማስታወስ የሚባል ነገር የለም፡፡ ቶሎ ትረሳለህ፡፡ 

‹‹ምን ያህል ጊዜ ቆየህ አውስትራልያ››

‹‹በሃሳብ ዘጠኝ ዓመት፣ በአካል አሥራ ስድስት ዓመት›› አለመረዳቴን ለመግለጥ አንገቴን ሊወድቅ እንደተዘጋጀ ብርጭቆ አወዛወዝኩ፡፡


‹‹ሱዳን ነበርኩ፡፡ ሱዳን ዘጠኝ ዓመት ቆየሁ፡፡ እዚያ እያለሁ በተስፋ አውስትራልያ ነበርኩ፡፡ ነገ ትሄዳላችሁ፣ አልቋል፤ ተጠናቋል፤ ፎርም ሙሉ፤ ተዘጋጁ፤ አሻራ ስጡ፤ ፎቶ ተነሡ ስንባል ዘጠኟን ዓመት ጠጣናት፡፡ እኛስ ይሁን በልጅነታችን ወጥተን ነው፡፡ አረጋውያን አባቶች ነበሩ እዚያ፡፡ ስደትና እብደት ካረጁ በኋላ አያምርም፡፡ የአብርሃም ቤት አዛውንቶች ሲባል ሰምተሃል?››

‹‹አልሰማሁም›› አልኩት፡፡

ቀጠለ፡፡ ‹‹እነዚህ አዛውንቶች ከ1966 ዓም ጀምሮ በኢዲዩ፣ በከፋኝ፣ በምናምን እየተደራጁ ሲዋጉ የኖሩ ናቸው፡፡ በኋላ ግን ሁሉም ነገር አልሆን አላቸው፡፡ አረጁ፡፡ መጀመሪያ በተለያዩ ቦታዎች፤ በኋላ ደግሞ አብዱል ረከም በሚባል የስደተኞች ካምፕ ውስጥ ከሃያ ዓመታት በላይ በሱዳን አሳለፉ፡፡ በመጨረሻም ከዛሬ ሰባት ዓመት በፊት ወደ 350 የሚጠጉ አዛውንቶች አውስትራልያ መጡ፡፡ መንግሥት ጡረታ ይሰጣቸዋል፡፡ ቋንቋው ግን መከራ ያሳያቸዋል፡፡ ቤት የመጣ ፖስታ ለማንበብ፣ ከማኅበራዊ አገልግሎት ሠራተኞች ጋር ለመግባባት ችግር አለ፡፡ አውስትራልያ ብር እንጂ ቋንቋ አትረዳ፡፡

የዘመድ ሰላምታ ሲመጣ ደብዳቤ

አንብቡልኝ ብዬ ለሰው አስነብቤ – የሚል ዘፈን ትዝ ይልሃል (በዜማ ነው ያለልኝ) እዚህ ተወዳጅ ዜማ ነው፡፡››

‹‹እዚህ ሀገር ከሱዳን የመጡ ይበዛሉ ልበል፡፡››

‹‹ልክ ነህ፤ በተለይ በኢሕአፓና በኢዲዩ ጊዜ ወጥተው፤አሥርና ሃያ ዓመት ሱዳን ኖረው የመጡ ናቸው አብዛኞቹ፡፡ ያልተቀየጠ ንጹሕ የኢሕአፓ ዘር እዚህኮ ነው ያለው፡፡ ጓድ ሲባባሉ ትሰማቸዋለህ፡፡ 

‹‹ ለመሆኑ ግን ከወጣህ በኋላ ወደ ሀገር ተመልሰህ ታውቃለህ?››

‹‹አንድ ጊዜ ብቻ››

‹‹ምነው፤ ጥፊም ይደገማል ይባል የለ እንዴ››

‹‹ታክሲ ነጅ ከሆንክ መደጋገምህ አይቀርም››

ታክሲው አያደርሳቸው››

‹‹ትርፊክ እየጣስክ ትነዳ ትነዳና ነጥብ ትሰበስባለህ፤ ከዚያ ወደ ዘጠኝ አካባቢ ስትደርስ መንጃ ፍቃድህን ነጥቀው እንዳትነዳ ይሉሃል፡፡ እዚህ ሀገር እንዴት ትዘልቀዋለህ፡፡ ሀገር የናፈቀህ መስለህ ኢትዮጵያ ትሄድና አንድ ሦስት ወሯን ቅጣት እዚያ ታሳልፋታለህ፡፡ ‹ለዕረፍት የመጣ ፍቅር›› በሚለው ፋንታ ‹ለዕረፍት የመጣ ሾፌር›› የሚል ፊልም ሠርተህ ትመለሳለህ፡፡››

ቢሆንም አገር አይደል››

‹‹ወዳጄ ሀገር ቤት ደርሶ የመጣና ቤቱ የተቃጠለበት አንድ ነው››

‹‹እንዴት››

‹‹ሙልጭህን ነዋ የምትቀረው፡፡ እዚያ ዝንጥ እያለ የምታየው ዳያስጶራ ሁሉ ከሀገሩ ሲመለስ ስልክ አያነሣ፣ ከሰው አይገናኝ፣ ኢሜይል አይከፍት፤ ይመንናል፡፡ ከሆስፒታል መውጣት በለው፡፡ በተለይ ኢምፖርት ሊያደርጉ የሚሄዱትማ››

‹‹ምንድን ነው ኢምፖርት የሚያደርጉት››

(ይቀጥላል)

ካሮላይን ስፕሪንግስ፣ ሜልበርን፣ አውስትራልያ

የኢትዮጵያን ነጻነት ስናስብ ልንዘክራቸው የሚገቡ፣ ለሀገሪቱ ደማቸውን ያፈሰሱ፣ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የታገሉ፤ ለነጻነቷ ሲሉ ከገዛ መንግሥታቸው ጋር የተሟገቱ፣ ዕውቀታቸውንና ገንዘባቸውን የከሰከሱ አያሌ የሌላ ሀገር ሰዎች አሉ፡፡ በተለይ ዛሬ ኢትዮጵያዊነት ቆሻሻ እንደ ነካው ልብስ በሚገፋበት ጊዜ ለኢትዮጵያዊነታችን ዋጋ የከፈሉትን ኢትዮጵያውያን ያልሆኑ ሰዎች ማስታወስ ግድ ይለናል፡፡

እዚህ አውስትራልያ መጥቼ ካገኘኋቸው መጻሕፍት አንዱ ‹ተልዕኮ 101 – Mission 101› የተባለ ዱንካን ማክናብ(Duncan Mcnab) በተባለ ሰው የተጻፈ መጽሐፍ ነው፡፡ ማክናብ መርማሪ(detective) ፖሊስ፣ የግል የምርመራ ሥራ (Investigator) ባለሞያ፣ ደራሲና ጋዜጠኛ የነበረ አውስትራልያዊ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በእንግሊዝ ወታደራዊ ተልዕኮ ውስጥ በመሰለፍ ለኢትዮጵያ ነጻነት የታገሉ አራት አውስትራልያውያን ወታደሮች ታሪክ ቀርቧል፡፡ ከአራቱ አንዱ የዱንካን ማክናብ አጎት ነበረ፡፡

በዚህ መጽሐፍ ላይ ከአራቱ ወታደሮች ጋር ታሪኩ ተያይዞ የቀረበ አንድ ሌላ ሰው አለ፡፡ ይህ ሰው የተወለደው እኤአ ኖቬምበር 25 ቀን 1877 ዓም በደቡብ ብሪዝበን(አውስትራልያ) ነው፡፡ አያት ቅድመ አያቶቹ ትንግርታዊ ጉዞ የሚወዱ(adventurers) ነበሩ፡፡ አያቱ ከእንግሊዟ ዌልስ በ1800ዎቹ ነበር ወደ አውስትራልያ የገባው፡፡ በምሥራቅ አውስትራልያ ከ117ሺ ሄክታር በላይ መሬት የነበረው ሀብታም አሳራሽ ነበረ፡፡ በኋላ ግን ወደ እንግሊዝ ተመልሶ በሄርፎርድ ሻየር ኑሮውን ቀጠለ፡፡ ልጁን አርኖልድንም በአዳሪ ትምህርት ቤት አስተማረው፡፡

በ1896 አርኖልድ እንግሊዝን ተወና ወደ አውስትራልያ መጥቶ በቤተሰቡ እርሻ ላይ መሥራት ጀመረ፡፡ በከተማ በሚገኘው ዘመናዊ ቤት ከመኖር ይልቅ በገጠር በነበረው የገበሬዎች ቤት ውስጥ በመኖርና አኗኗሩን ሁሉ እንደ ገበሬዎቹ በማድረግ የተለየ ሕይወት የመኖርን ዘይቤ እንደ አያቶቹ ተካነበት፡፡ ‹ቋረኛው› አርኖልድ ዊንሆልት እንግዲህ የዚህ ሰው ልጅ ነበር፡፡

ዊንሆልት ሲፈጥረው የትግል ሰው ነው፡፡ መከራ ባለበት ቦታ ገብቶ መታገል የሚወድ፡፡ በ1899 እኤአ በደቡብ አፍሪካ የቦር ጦርነት ሲፈነዳ የቤተሰቡን ሀብት ትቶ እንዲያውም ለፈረስ መግዣ እንዲሆነው የተወሰነውን ሽጦ በኩይንስ ላንድ ጦር ወስጥ በመመዝገብ በ1900 ወደ ደቡብ አፍሪካ ሄደና ለለስምንት ዓመት በውጊያ ላይ ቆየ፡፡ ጦርነቱ ሲፈጸምም ወደ አውስትራልያ ተመልሶ የቤተሰቡን ሀብት ማስተዳደር ጀመረ፡፡ ከሀብቱ ጎን ለጎን በኩዊንስ ላንድ ፖለቲካ ውስጥ ንቁ ተሳታፊ በመሆን ለግዛቲቱ ሕግ አውጭ ምክር ቤት በ1909 ተመርጦ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ በ1913 እኤአ ወደ አፍሪካ ተመልሶ በደቡብና በደቡብ ምእራብ አፍሪካ ውጊያዎች ላይ በፈቃደኛነት ተሳትፏል፡፡ እንዲያውም በናሚቢያ በረሃ እያለ በአንበሳ እስከ መነከስ ደርሶ ነበር፡፡

በዚህ መካከል በ1928 ዓም ሞሶሎኒ ኢትዮጵያን ወረረ፡፡ ዊንሆልት ይህ ነገር በጣም ነበር ያሳሰበው፡፡ በአንድ በኩል የኢትዮጵያ መወረር፤ በሌላ በኩል ሞሶሎኒ በአፍሪካ ለነበሩ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛቶች አደጋ መሆኑ ልቡን ገዝቶታል፡፡ ጦርነቱን በቅርብ ለመረዳት እንዲችል የብሪዝበኑ ኮርየር ሜይል ጋዜጣ የጦርነት ሪፖርተር አድርጎ ወደ ምሥራቅ አፍሪካ እንዲልከው አደረገ፡፡ በኖቬምበር 22 ቀን 1935 እኤአ ከአውስትራልያ ወደ አፍሪካ በመርከብ አመራ፡፡ በኤደን በኩል አድርጎ ጅቡቲ፣ በጅቡቲ በኩልም በባቡር ተሣፍሮ አዲስ አበባ ገባ፡፡ ኢምፔሪያል ሆቴልም ዐረፈ፡፡

አርኖልድ ዊንሆልት

ዊንሆልት በኢትዮጵያ አርበኞች የአልበገር ባይነት ውጊያ መንፈሱ ተማርኮ ነበር፡፡ እርሱ በደቡብ አፍሪካ፣ በናሚቢያና በአንጎላ የተዋጋው የደፈጣ ውጊያ ስልት በኢትዮጵያ አርበኞች ሲተገበር ማየቱ እንዲቀላቀላቸው ይገፋፋው ነበር፡፡ ዊንሆልት ስለ ደፈጣ ውጊያ አንብቧል፣ ሠልጥኗል፤ በተግባርም ሠርቶበታል፡፡ የደፈጣ ውጊያም ይማርከዋል፡፡ ይህንን የአርበኞች ውጊያ ለመረዳትና ለመዘገብ ግን አልቻለም፡፡ ጣልያኖች ጋዜጠኞች ከአዲስ አበባ እንዲወጡ አይፈቅዱም ነበር፡፡
ዊንሆልት ይህ ነገር መንፈሱን አላረካው ሲል የቀይ መስቀል ሾፌር ሆኖ በመቀጠር ወደ ገጠሮች ለመሄድ ወሰነ፡፡ በ1936 እኤአ የፈለገውን ሥራ አገኘው፡፡ በዚህ ሥራው አማካኝነት በአዲስ አበባ ለነበረው የእንግሊዝ ሌጋሲዮን መረጃ ከማቀበሉም በላይ ጦርነቱን በቅርብ ለመረዳትም ቻለ፡፡ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ጦርነቱ ዜና መሆኑ አበቃ፡፡ ዊን ሆልትም ወደ አውስትራልያ ተመለሰ፡፡

ዊንሆልት በአንዳንድ ኢትዮጵያውያን ጠባይ ባይደሰትም የኢጣልያ ወረራ ግን ትክክል አልነበረም ብሎ ያስብ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበሩት ኃያላን ሀገሮች ለኢትዮጵያ ጥያቄ ተገቢ መልስ አለመስጠታቸውም አሳዝኖታል፡፡ ይህንን ስሜቱን ኮርየር ሜይል ለተሰኘው ጋዜጣ እየጻፈ ቢልክም ዋና አዘጋጁ ግን ለማተም ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ዊንሆልት ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሞሶሎኒንና የእንግሊዙን ጠቅላይ ሚኒስትር ቻምበርላይንን ያወግዝ ነበር፡፡ ጋዜጦች የነፈጉትን ዕድል የተለያዩ መድረኮችን በማዘጋጀት ይወጣ ነበር፡፡ ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ስለ ኢትዮጵያ ይናገራል፡፡

በ1937 እኤአ ዊንሆልት አውስትራልያን ለቅቆ እንደገና ወደ የመን አመራ፡፡ በየመን ዋና ከተማ ኤደን ያገኛቸውን የእንግሊዝ ታላላቅ ወታደራዊ ባለ ሥልጣናትንም ኢትዮጵያን ለማገዝ እንግሊዝ ጦር ማዝመት እንዳለባት መወትወት ጀመረ፡፡ በተለይም የአርበኞችን የደፈጣ ውጊያ በመጠቀም ጣልያንን ሰላም መንሣትና በመጨረሻም ማስወጣት አለብን የሚለውን ሃሳቡን በተደጋጋሚ ለማሳመን ይጥር ነበር፡፡ የየመን ቆይታው አልሳካ ሲለውም ወደ ለንደን አምርቶ ከእንግሊዝ የዲፕሎማሲና ወታደራዊ ባለሥልጣናት ጋር በሃሳቡ ተነጋገረ፡፡ ማንም ግን ትኩረት ሊሰጠው አልወደደም፡፡ ዊንሆልት በዚያ እያለ ታዋቂዋ የኢትዮጵያ ወዳጅ ሲልቭያ ፓንክረስት ለምታሳትመው New Times – Ethiopian News ዋና የጽሑፍ አበርካች ሆኖ ነበር፡፡

 በተለይም በአፕሪል 16 ቀን 1938 እንግሊዝና ጣልያን ‹የአንግሎ ጣልያን› ስምምነትን ሲፈራረሙ ዊንሆልት በጣም አዘነ፡፡ ለንደንንም ለቅቆ ወደ የመን ተመለሰ፡፡ ከየመንም አገሩ አውስትራልያ ገባ፡፡ በየሄደበት ሁሉ ስለ ኢትዮጵያ ጉዳይ መናገርና መቀስቀስም ዋና ተግባሩ ሆነ፡፡ የኢትዮጵያ ጉዳይም የመተዳደርያ ሥራውን እስከ ማስረሳት አደረሰው፡፡

በዚህ መካከል እንግሊዝና ጀርመን እየተቃቃሩና ወደ ጦርነት እያመሩ ሄዱ፡፡ የአውስትራልያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሮበርት ሜንዝየስም በጀርመን ላይ ጦርነት ዐወጀ፡፡ ዊንሆልት ይህንን እንደ መልካም አጋጣሚ ወሰደው፡፡ ፊቱንም ወደ አፍሪካ ለመመለስ እንዲችል አበቃው፡፡ ሴፕቴምበር 27 ቀን በ1935 እኤአ በ62 ዓመቱ ከአውስትራልያ ለቅቆ ወደ ሲንጋፖር፣ ከዚያም ወደ ኤደን አመራ፡፡ በዚያም አንድ አፓርትመንት ተከራይቶ ዐረብኛና አማርኛ የሚችል ተርጓሚ ቀጠረ፡፡ ለሲልቭያ ፓንክረስት የሚልከውን ጽሑፍ ሳያቋርጥ ያገኛቸውን አካላት ሁሉ የኢትዮጵያ አርበኞችን ስለመርዳትና በእነርሱም አማካኝነት ጣልያንን ድል ስለማድረግ ያማክር ነበር፡፡

ይህ ጥረቱ ውጤት በማምጣቱ የተነሣም በሜይ 1940 ሃሳቡን ተግባራዊ ለማደረግ የሚያስችል ደብዳቤ ከእንግሊዝ ወታደራዊ ባለ ሥልጣናት ደረሰው፡፡ ዊንሆልትም እየፈነደቀ በ62 ዓመት እድሜው እንደገና ወደ ውትድርና ተመለሰ፡፡ በጁን 17 ቀን 1940 እኤአ ከየመን ወደ ሱዳን ካርቱም በረረ፡፡

ምንም እንኳን ለንደን ለሚገኙት ለቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ የተገለጠ ነገር ባይኖርም እንግሊዞች ግን እያሠጋቸው የመጣውን የጣልያኖችን ኃይል ከምሥራቅ አፍሪካ ለማስወጣት ምሥጢራዊ ዕቅድ በማዘጋጀት ላይ ነበሩ፡፡ ለዚህ ደግሞ የኢትዮጵያን አርበኞች በማገዝ ጣልያኖችን ሰላም መንሣትና በመጨረሻም እንዲወጡ ማደረግ በብዙዎቹ ባለሞያዎቻቸው የታመነበት ዕቅድ ሆነ፡፡ ይህ ዕቅድ ዊንሆልት በተደጋጋሚ ሲወተውተው የነበረ ዕቅድ ነበረ፡፡ እንግሊዞች ይህንን ዕቅድ የተሳካ ለማድረግ በሕንድና በመካከለኛው ምሥራቅ ያገለገለውን በተለይም ደግሞ በምድረ ፍልስጤም እሥራኤልን በመርዳት የተሳከለት ሥራ የሠራውን፣ ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ማብቃት በኋላም ወደ ኢትዮጵያ ክርስቲን ከምትባለው ባለቤቱ ጋር መጥቶ ከአዲስ አበባ በስተ ሰሜን ኑሮ የጀመረውን ዳን ሳንፎርድን ነበር የመረጡት፡፡ ሳንፎርድ ስለ ኢትዮጵያ ማወቅ ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱ ይቆረቆር የነበረ፤ ከብዙዎቹ የዘመኑ መሳፍንትና መኳንንት ጋርም መልካም ግንኙነት የነበረው፤ በንጉሠ ነገሥቱ ዘንድም መታወቅንና መከበርን ያተረፈ ሰው ነበር፡፡

ሳንፎርድና(ግራ) ዐፄ ኃይለ ሥላሴ በደምበጫ ግንባር(ጎጃም)
ዳን ሳንፎርድ አዲስ አበባን ለቅቆ ወደ እንግሊዝ የተመለሰው ጣልያኖች ኢትዮጵያን ሲወርሩ ነበር፡፡ አሁን ከጡረታ ተጠርቶ የዚህ የኢትዮጵያ ተልዕኮ መሐንዲስ እንዲሆን ተደረገ፡፡ መጀመሪያ ወደ ካይሮ ከዚያም ወደ ካርቱም በመምጣት ከሌሎች የውትድርና ባለሞያዎች ጋር ዕቅዱን ነደፈ፡፡ ዊንሆልት ካርቱም የደረሰው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ ዳን ሳንፎርድ በጎጃም በኩል ወደ ኢትዮጵያ በመግባት ከአርበኞች ጋር ሆኖ ጣልያንን ለመውጋት ሲያስብ በደቡብ አፍሪካው የደፈጣ ውጊያ ጊዜ አንድ እጁ ጉዳት የደረሰበት ዊንሆልት እዚያው ሆኖ እርሱም ከአርበኞች ጋር ተቀላቅሎ የደፈጣ ውጊያ ለመቀጠል እየተሟሟቀ ነበር፡፡

ሳን ፎርድ በገለባት በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለመዝለቅ የነበረው ዕቅድ ጣልያኖች ገለባትን በመያዛቸው ምክንያት ከመተማ 19 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደ ምትገኘው ሌሞና ተዛወረ፡፡ ጣልያኖችና ባንዳዎች ከቋራ እስከ መተማ ያለውን ቦታ መሽገውበት ነበር፡፡ ከእንግሊዝ የምሥራቅ አፍሪካ እዝ የመጨረሻውን መመሪያ ሲጠባበቅ የነበረው ኮሎኔል ሳንፎርድ በኦገስት 6 ቀን ዶቃ ከሚገኘው ካምፕ 54 በቅሎ፣ 36 አህዮች፣ ስድስት ገመድ አልባ መገናኛዎች፣ 13303 ጠመንጃዎች፣ 3 ሪቮልቨሮች፣ 30 አሮጌ ጠመንጃዎች፣ ከአራት የእንግሊዝ ወታደሮች፣ ከአንድ ሐኪምና ከአንድ የራዲዮ ሠራተኛ ጋር ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ተነቃነቀ፡፡ ሳንፎርድ ዊንሆልትን በዶቃ ካምፕ ትቶት ነበር የመጣው፡፡

በአንድ በኩል ይህ የተደረገው እነ ሳን ፎርድ መንገዱን ከጠረጉ በኋላ ዊንሆልት እንዲከተላቸው በማሰብ ነው የሚሉ አሉ፡፡ ያን ጊዜ ዊንሆልት ገና የመጓጓዣ አጋሰሶችን አላዘጋጀም ነበርና፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የዊንሆልት በዶቃ ካምፕ መገኘት ከሌላኛው መኮንን ከሮኒ ክሊችሌይ ጋር አለመጣጣም አስከትሎ ነበር፡፡ የመረጃ ሰው የሆነው ክሊችሌይ ዊንሆልት አርጅቷል ብሎ አስቧል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ለመዝለቅ ያለውን ጉጉትና ከሲልቭያ ፓንክረስት ጋር ስለሠራው ሥራ ደጋግሞ ማውራቱን አልወደደውም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እርሱ ራሱ በዚያ ጊዜ ጥቂት በእድሜ ገፍቶ የነበረው ሳን ፎርድ ዊንሆልትን ‹አርጅቷል› ብሎ በማሰብ በተልዕኮው ውስጥ ማካተት አልፈለገም ነበር፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ዊንሆልት አንድ እጁ በሚገባ አይሠራም፡፡

ዊንሆልት ግን ሁሉንም ትቶ 11 አህዮችን፣ ስድስት የታጠቁ የኢትዮጵያ ወታደሮችንና አንድ ሱዳናዊ  ምግብ አብሳይ አዘጋጀ፡፡ በ1940 እኤአ፣ ኦገስት 31 ቀን ሳን ፎርድ የሄደበትን መንገድ በመተው ዊንሆት ከመተማ በስተደቡብ ወደ ቋራ አቅጣጫ የሱዳንን ድንበር ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ ጀመረ፡፡ በመንገድ ላይ የተወሰኑትን ኢትዮጵያውያን ወታደሮችና ሱዳናዊውን አብሳይ ቀነሳቸው፡፡ ሁለት አገልጋዮችንና ሦስት አህዮችን ብቻ በመያዝ ጠመንጃውን እንደ አገሬው ሰዎች በትከሻው ወደ ታች አጋድሞ ጉዞ ቀጠለ፡፡ ከመነሣቱ በፊት ሊሄድ ያሰበበት መንገድ ለጣልያን ያደሩ ባንዳዎች የሚገኙበት አደገኛ መንገድ መሆኑን ተነግሮት ነበር፡፡ እርሱ ግን አልተቀበለውም፡፡ እንዲያውም መጣቢያ በምትባል ጣቢያ 50 የጣልያን ወታደሮችና 300 የአካባቢው ተወላጅ ባንዶች ካምፕ መሥርተው አካባቢውን እየቃኙ ነበር፡፡
ጉዞ ወደ ኢትዮጵያ
ዊንሆልት ኦገስት 31 ከሌሎቹ የእንግሊዝ መኮንኖች ተለያይቶ በቋራ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ከዘለቀ በኋላ ድምፁ ጠፋ፡፡ ሳንፎርድም ዊንሆልት ወደ እርሱ ዘንድ አለመድረሱን ገለጠ፡፡ በገለባትና በካርቱም የሚገኙ የእንግሊዝ ሚሲዮኖች ዊንሆልት የት እንደገባ ለማወቅ አልቻሉም፡፡ የዊንሆልት ዜና ከተሰማ 15 ቀናት አለፉ፡፡ ሴፕቴምበር 15 ቀን 1940 ከዊንሆልት ጋር አብረው ሄደው የነበሩ ሁለት ሰዎች  በዶቃ ካምፕ ተገኙ፡፡ በካምፑ የነበሩት ቴሲገርና ላውሬ የተባሉ ሁለት የእንግሊዝ መኮንኖች የዊንሆልትን ዜና ጠየቋቸው፡፡ ኢሳ አቡ ጂያር እንደተናገረው ከሆነ ይመራቸው የነበረው ሰው የጉሙዝን አካባቢ እያቋረጡ እያሉ ጠፋባቸው፡፡ በዚህም ምክያት በመጣቢያ አካባቢ ካምፕ ሠርተው ተቀመጡ፡፡ በዚህ መካከልም አንድ ቀን በድንገት ከአራቱም አቅጣጫ ተኩስ ተከፈተባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ዊንሆልት ጠመንጃውን ለአስተርጓሚው አሸክሞት ነበር፡፡

ሁለቱ አገልጋዮቹ ተኩሱን ሲሰሙ እየሮጡ በየአቅጣጫው ጠፉ፡፡ መሣሪያ ያልያዘው ዊንሆልት ብቻውን ቀረ፡፡ ከዚህ በኋላ ያለውን ኢሳ አቡ ጂያር የሚያውቀው ነገር አልነበረም፡፡ እርሱ አምልጦ ወደ ዶቃ ገብቷል፡፡ ሁለቱ የእንግሊዝ መኮንኖች ይህንን ሪፖርት ሲያስተላልፉ ሌላ ዘገባ ከገለባት መጣላቸው፡፡ ‹‹ሌፍትናንት ዊንሆልት በብዙ ችግር ወደ ሰራቆ ደርሷል፡፡ ፊታውራሪ ወርቁ ስንቄም አስፈላጊውን ነገር ረድተውት ወደ ጎጃም አምርቷል›› ይላል፡፡ ነገር ግን ዊንሆልት ወደ ጎጃም ዘልቆ ሊታይ አልቻለም፡፡ በኋላ እንደተረጋገጠውም የገለባቱ ዘገባ ትክክል አልነበረም፡፡

ከወራት በኋላ እንግሊዞች በአካባቢው ባደረጉት አሰሳ ዊንሆልት ይጠቀምበት የነበረውን  ሄልሜት፣ የተበጫጨቁ ልብሶቹንና ይዞት የነበረውን ቦርሳ(ኪት) አገኙት፡፡ አሳሽ ጓዱም ዊንሆልት መጀመሪያ ተመትቶ ወደ ጫካ በመግባት በዚያው ሳይሞት እንዳልቀረ ገመተ፡፡

ጦርነቱ ከተጠናቀቀ በኋላ የዊንሆልት ባለቤት በካርቱም ያለውን የእንግሊዝን ሚሲዮን የባሏን መጨረሻ እንዲያሳውቃት ጠይቃ ነበር፡፡ በጁላይ 8 ቀን 1941 እኤአ ከጋላባት የተነሡ እንግሊዝ ወታደራዊ አሳሾች ዊንሆልት የሄደበትን መንገድ ተከትለው እነዚያ ሁለት አብረውት የተጓዙ ሰዎች ካምፕ ሠራንበት ወዳሉት ቦታ ተንቀሳቅሰው ነበር፡፡ በአካባቢው የተገኙ መረጃዎች እንደጠቆሙት ጣልያኖች የዊንሆልትን መምጣት በማወቃቸው በመንገዱ ተከትለውታል፡፡ በመጨረሻም ካምፑን በመውረር ተኩስ ሲከፍቱባቸው ዊንሆልትና አብረውት የነበሩት ሰዎች ካምፑን ጥለው ጠፉ፡፡ ጣልያኖችና ባንዶችም ወደ ካምፑ ገቡ፡፡

ከዓይን እማኞችና በጊዜው ከነበሩ የአካባቢው ሰዎች ያገኘውን መረጃ ይዞ አሳሹ ጓድ ከመጣብያ የአራት ወይም የአምስት ሰዓት መንገድ ወደሚርቀውና ከሺንፋ ወንዝ አጠገብ ወደነበረው የዊንሆልት ካምፕ ቦታ ደረሰ፡፡ በአካባቢው በተደረገው ምርመራ የአህዮች አጥንት፣ የተተኮሱ ጥይቶች ቀለሃዎችና የጫማ ቅሬቶች ተለቀሙ፡፡ በአቅራቢያውም የጥርስ መፋቂያና ቦት ጫማ ተገኘ፡፡ ካምፑ ነበረበት ከተባለው 300 ያርድ ርቀት ላይም በመበስበስ ላይ የነበሩ የሰው አጥንቶች ታዩ፡፡ ምናልባትም የቆሰለው ዊንሆልት እዚህ ድረስ ተጉዞ ይሆናል ለሞት እጁን የሰጠው፡፡

ካርቱም የሚገኘው የዊንሆልት የመታሰቢያ ሐውልት 
ይህ ሪፖርት ሲድኒ ሲደርስ የኩዊንስ ላንድ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ኦክቶበር 10 ቀን 1941 እኤአ የዊንሆልትን መሞት በይፋ ዐወጀ፡፡ ቋረኛው የአውስትራልያ ሰውም የኢትዮጵያን ነጻነት ሳያይ ቋራ ላይ ቀረ፡፡ አንደኛው ቋረኛ(ዐፄ ቴዎድሮስ) ለእንግሊዝ እጄን አልሰጥም ብሎ በጀግንነት ሞተ፡፡ ሌላኛው ቋረኛም ኢትዮጵያን ነጻ አወጣለሁ ብሎ በሀገሬው ባንዶች ተገደለ፡፡ ኢትዮጵያ የምትባለው ሀገር እንዲህ ነጭ ከጥቁር ዋጋ ከፍሎባታል፡፡ ኢትዮጵያ እንግሊዞች፣ ኩባዎች፣ አውስትራልያዎች፣ ዐረቦች፣ አይሁድ፣ ሱዳኖች፣ ሩሲያዎች፣ አሜሪካኖች፣ ግሪኮችና ሌሎች ዋጋ ከፍለው ሀገር ያደረጓት ሀገር ናት፡፡ እንኳን የተወለዱባትን ያወቋትን ሰዎች ሕይወት የምታስገብር ሀገር፡፡

 ከፐርዝ ወደ ሜልበርን፣ ኳንታስ አውሮፕላን ላይ

አሁን አብዛኛው አውስትራልያ የገባ ኢትዮጵያዊ በሚገኝባት የሜልበርን ከተማ ውስጥ አበሻው ሰብሰብ ብሎ በሚኖርባትና በሚሠራባት ፉትስክሬይ በተባለችው መንደር እንገኛለን፡፡ ይህች የሜልበርን ምዕራባዊ ቀበሌ የሆነች መንደር ጥንት የኤስያውያን መናኸርያ ነበረች ይባላል፡፡ ዛሬ ግን ዋናዋ የአፍሪካውያን ስደተኞች መሰባሰቢያ ናት፡፡ በዚህች ከ74000 ትንሽ ከፍ የሚል ሕዝብ በሚኖርባት መንደር ውስጥ ከ135 ሀገሮች የመጡ ስደተኞች ይኖሩባታል፤ ከ85 ቋንቋ በላይ ይነገርባታል፡፡ እንዴው መርካቶ በሏት፡፡

በአውስትራልያ ታሪክ የመጀመሪያው የእንጀራ መሸጫ ሱቅ የተከፈተው እዚህ ነው፡፡ በነገራችን ላይ እዚህ ሀገር እንጀራ በዋናነት ከስንዴ ወይም ከሩዝ ዱቄት ተቦክቶ የማሽላ ዱቄት ይቀላቀልበታል፡፡ የታደሉት ደግሞ ከሀገር ቤት የመጣ የጤፍ ዱቄት ለአመል ይጨምሩበታል፡፡ ስፋቱ የአገር ቤት እንጎቻ የሚያህል ሲሆን ውፍረቱ የሰንበት ቂጣ ታናሽ ወንድም ነው፡፡ ኮከብ የመሰለ ዓይን ባያገኝም፣ ሞጭሟጫ ከመባል ለጥቂት ይተርፋል፡፡ በብዛት የሚጋገረው ከብረት በተሠራ ምጣድ ነው፡፡ አልፎ አልፎ ግን ከሀገር ቤት የሸክላ ምጣድ የሚያመጡ አሉ፡፡ ሳይሰበር ከደረሰላቸው፡፡

በፉት ስክሬይ ከደርዘን በላይ የኢትዮጵያውያን ሱቆች፣ ከአምስት በላይ ምግብ ቤቶች እንዳሉ ይነገራል፡፡ በአካባቢው ስትዘዋወሩ ቢያነጥሳችሁ ‹ይማርህ› የሚል አታጡም ይባላል፡፡ ብዙ ኢትዮጵያውያን እናቶችና አባቶች ስለሚዘዋወሩበት፡፡ በርግጥ ወጣቶቹና ጎልማሶቹ እንዲህ ያለ ነገር አያውቁም፡፡ የሚገርማችሁ እንዲያውም እዚህ አካባቢ አበሻና አበሻ ሲገናኝ ቁጣ እንጂ ሰላምታ አይሰጣጥም፡፡ ሁለቱም ፊታቸውን ኮስተር አድርገው ነው የሚተላለፉት፡፡ እኔ እንዲያውም ‹እዚህ ሀገር የመጣው ያኮረፈው ተመርጦ ነው እንዴ› ብዬ ነበር፡፡

በፉት ስክሬይ የሚጠፋ ቅመማ ቅመም የለም፡፡ በተለይም ሕንድ ሱቅ ውስጥ በሀገራችን የጠፋው ቅመም ሁሉ ይገኛል፡፡ ሞያ በሜልበርን በሽ በሽ ነው፡፡ በርበሬ ከሀገር ቤት ለማስመጣት የአውስትራልያ የምግብ ሕግ ሲያስቸግር እዚሁ ሌላ በርበሬ ተፈጥሯል፡፡ ከሕንዶች ሱቅ የሚገዛ የሚያቃጥል ቀይ ቃሪያ አለ፡፡ እርሱን በኮረሪማ መፍጫ መፍጨት ነው፡፡ ከዚያ ደግሞ ቅመማ ቅመሙን ለብቻ ፈጭቶ መጨመር፡፡ በመጨረሻም አውስትራልያ ሠራሽ ምርጥ ድልህ ይሆንላችኋል፡፡

 አንድ ወዳጃችን ‹ሽሮ እኛን ስላሳደገች በክብር ጡረታ ወጥታ ትቀመጥ› ቢልም ከሀገር ሲወጡ አንዱ የሚናፍቀው ግን ሽሮ ነው፡፡ በአውስትራልያ ልዩ የሆነ የሽሮ አዘገጃጀት ተፈጥሯል፡፡ የባቄላው ዱቄት ከሕንድ ሱቅ ይገዛል፡፡ ከዚያም አመስ አመስ ይደረጋል፡፡ ለቅመማው አስፈላጊ የሆነውን ቅመምም ሕንዶቹ ያመጡታል፡፡ እርሱንም በቡና መፍጫ ፈጭቶ በመጠኑ ማመስ ነው፡፡ ከዚያም ሁለቱን በባለሞያ እጅ ደባልቆ ምርጥ የውጭ ሀገር ሽሮ ማግኘት፡፡ ችግር ብልሃትን ይፈጥር የለ፡፡

   ለኢትዮጵያውያን እዚህ አንዱ ፈተና ከሀገር ቤት ባህላዊ ምግቦችን ማስመጣት ነው፡፡ የሀገሩ ሕግ ጥብቅ ስለሆነ፡፡ ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ ግን እንደ ካልዲ(የቡናን ፍሬ ያገኘው እረኛ) አዳዲስ ቅጠላ ቅጠሎችን የሚያገኙ ኢትዮጵያውያን እዚህ ሞልተዋል፡፡ አንድ ቀን ነው አሉ፡፡ መቼም እኛ ታሪክን በጊዜና በሰዓት የመመዝገብ ችግር አለብን፡፡ (ተረቱም ታሪኩም ከዕለታት በአንድ ቀን ብሎ ነው የሚጀምረው) አንዲት የሀገሬ ሰው በግቢዋ ውስጥ ስትዘዋወር አንድ የምታውቀውን ቅጠል የሚመስል ነገር ታያለች፡፡ ጠጋ ብላ ቆረጠችውና መዳፏ ላይ አሸችው፡፡ ልክ ነው፤ እርሱ ነው፡፡ ወስዳ ለጓደኛዋ አሳየቻት፡፡ ሁለቱም ርግጠኞች ሆኑ፡፡ ጉዳዩን ወደ ልጅቱ እናት ‹ሪፈር› አደረጉት፡፡ እርሳቸውም እየተገረሙ ‹እርሱ ነው› አሉ፡፡ ለካስ ጌሾ ኖሯል፡፡ ጠላ ለመጥመቅ ችግር የነበረው ጌሾ በአውስትራልያ ምድር በቅሎ ተገኘ፡፡ ዛሬ በብዙ ኢትዮጵያውያን ግቢ ውስጥ ጌሾ በቅሎ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡

በዚህች ምድር በቅሎ የተገኘው ግን ጌሾ ብቻ አይደለም፡፡ መቼም አገር ደግ ነገር ብቻ አታበቅል፡፡ አንድ ወዳጃችን ሁል ጊዜ አንድ ቦታ እየሄደ ቅጠል ሸምጥጦ ሲወጣ ይታያል አሉ፡፡ መጀመሪያ አካባቢ ማንም ከቁም ነገር አልወሰደውም ነበር፡፡ በኋላ ግን ሸምጣጩ በዛ፡፡ የአካባቢው ሰዎችም ግራ ገባቸው፡፡ በከተማዋ ውስጥም ወሬው ተባዛ፡፡ የሚሸመጠጥበት ቦታም በአንዳንድ ሰዎች መዘውተር ጀመረ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ከሥሩ እየነቀሉ ወስደው በጓሯቸው ተከሉት፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ የአውስትራልያ ፖሊሶች ጉዳዩን ሰሙትና ክትትል አደረጉ፡፡ ለካስ ያ በወፍ ዘራሽ በቅሎ አገር እየተራኮተ የሚሸመጥጠው ጫት ኖሯል፡፡ ፖሊሶቹ እዚያ ቦታ የነበረውን መድምደው አጠፉት፡፡ ችግሩ ግን እነርሱ ሳይደርሱ በፊት በየግቢው ተዛምቷል፡፡ አንዳንድ ቤት ስትሄዱ ጫት በኩራት በቅሎ ታዩታላችሁ፡፡

ፉት ስክሬይ በአበሾች ዘንድ ከምትታወቅበት ሀብቷ አንዱ ምርጥ የሆነ ቁርጥ ሥጋ መሸጫ ስለሆነች ነው፡፡ መቼም ቁርጥ እየበላን ቁርጥ ነገር አለመቻላችን የሚገርም ቢሆንም የሀገሬ ሰው የትም ቦታ ቢሄድ፣ ምንም ዓይነት ትምህርት ቢማር ሊያጣው የማይፈልገው ነገር ቢኖር ቁርጥ ሥጋ ነው፡፡ ከነአባባሉም ‹የተማረ ሰውና የተሳለ ቢላዋ ሥጋ አያጣም› አይደል የሚባለው፡፡ እዚህ ከተማ በጥሬ ሥጋ ሻጭነታቸው የታወቁ ቤቶች አሉ፡፡ ነጭ፣ ቀይ፣ ጎድን፣ ዳቢት፣ ሻኛ፣ ለቁርጥ፣ ለወጥ እያሉ የሚያስተናግዱ፡፡ እነርሱ ጋ ገብቶ አለበለዚያም ደግሞ ሰፈር ይዞ መጥቶ ቁርጥ በኅብረት መብላት እዚህ የተለመደ ነው፡፡ ከአውሮፓና ከአሜሪካ ወደ አውስትራልያ ዘመድ ለመጠየቅም ሆነ ለመዝናናት የሚመጡ ኢትዮጵያውያን በአውስትራልያ ቁርጥ ፍቅር ተነድፈው ነው የሚመለሱት፡፡ አንዳንድ የአውሮፓና የአሜሪካ ወዳጆቼ ጋር ስንጻጻፍ እንዲያውም ‹የአውስትራልያን ቁርጥ ሳትበላ እንዳትመጣ› ይሉኛል፡፡ እስቲ ቀምሼ እመሰክርለታለሁ፡፡

‹አይ እኔ ማን እንደነካው የማይታወቅ ሥጋ አልበላም› ለሚሉ አለያም ደግሞ ‹የተሸረፈ ጥርስ፣ ደልደል ያለም ላት አይቶ መርጦ ተከራክሮ መግዛት› ለሚያምራቸው ወደ ገጠሩ ክፍል ወጣ ማለት ነው፡፡ ከበግ አርቢ ገበሬዎች ጋር ምን የመሰለ የደብረ ብርሃን በግ ይገኛል፡፡ ማረዱን ባይፈቅዱላችሁም መባረኩን ይፈቅዱላችኋል፡፡ እነርሱ ደግሞ ገፍፈውና ቆራርጠው ይሰጧችኋል፡፡ ከዚያ በኋላማ ‹አቤት ባለፈው ለፋሲካ የገዛሁት ምን የመሰለ በግ› እያላችሁ ሾላ ገበያ የሄዳችሁ ማስመሰል ነው፡፡ 

ሜልበርን አውስትራልያ፡፡

7, 617, 930 ስኩዌር ኪሎ ሜትር በምታካልለው ሰባተኛ አህጉር፣ በስፋቷ የዓለማችን ስድስተኛ ሀገር በሆነችው አውስትራልያ ውስጥ እገኛለሁ፡፡  አንድ አህጉር አንድ ሀገር ሲሆን አውስትራልያ በዓለማችን ብቸኛዋ ትመስለኛለች፡፡ የሚገርመው ግን ይህንን የሚያህል ሰፊ ሀገር ውስጥ የሚኖሩት ሃያ ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ብቻ መሆናቸው ነው፡፡ ‹አይሆንም እንጂ ቢሆንማ› እንደሚባለው ቢቻል ኖሮ ከአውስትራልያ ይዤ ወደ ሀገሬ የምገባው የቤት መሥሪያ መሬት ነበር፡፡ እዚያ የወባ ክኒን የምታክል መሬት ለማግኘት የቀበሌ መታወቂያ፣ 10/90፣ 20/80፣ ባንክ ቤት፣ ወረፋ፣ ምዝገባ፣ ዕጣ፣ መከራ እያሳየን እዚህ መሬት የካንጋሮ መጨዋቻ ሆኖላችኋል፡፡ ‹አስወስጄ መጣሁ አስወስጄ› የሚለው ዘፈን ባህል ነውና እኛ የባሕር በራችንን አስወስደን ትንሷን ጅቡቲ ስንለማማጥ እንኖራለን፤ የዓለማችን ትልቋ ደሴት የምትባለው አውስትራልያ 34,218 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የባሕር ጠረፍ ባለቤት ናት፡፡ አውስትራልያ የሚለው ስም ከላቲኑ ‹‹አውስትራሊስ› የመጣ መሆኑንና ትርጉሙም ‹ደቡባዊ› ማለት እንደሆነ ይነገራል፡፡

በስድስት ክልሎችና በሁለት ልዩ ግዛቶች የተመሠረተችው ይህች ፌዴራላዊት ሀገር ራሳቸውን ‹አውሴ› ብለው የሚጠሩት የዛሬ ዋነኛ ነዋሪዎቿ ከመምጣታቸው በፊት ‹አቦርጅን›[አዳሙ ተፈራ የሚባል አውስትራልያ የሚኖር ደራሲ – ‹ኑር ተገኝ› ብሎ ጠርቷቸዋል፡፡] የተባሉ ጥንታውያን ሕዝቦች ይኖሩባት የነበረች ሀገር ናት፡፡ እነዚህ ከእስያ መጥተው ከብዙ ሺ ዓመታት በፊት የኖሩት ባላገሮቹ ዛሬ በሰሜናዊ አውስትራልያ በሚገኘው ‹የሰሜን ግዛት› በሚባለው ልዩ ክልል ውስጥ በብዛት ይገኛሉ፡፡ እንግሊዞች ወደዚች ሀገር ሲመጡ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ቁጥር ነበራቸው የሚባሉት አቦርጅኖች በደረሰባቸው ግፍና መከራ የተነሣ ቁጥራቸው መንምኗል፡፡ ለመሬታቸው ሲባል ተሰድደው፣ ተገድለውና በበሽታ እንዲያልቁ ተደርገው ሀገራቸውን አጥተዋል፡፡ በ1787 ዓም የተነሣውና መጤዎቹ ሆን ብለው ወደ አቦርጅኖች እንዲደርስ አድርገውታል የሚባለው ፈንጣጣ ብቻ ‹ዳሩግ› ከሚባሉት የአቦርጅን ጎሳዎች መካከል ዘጠና በመቶውን ፈጅቷቸዋል፡፡ [የኡጋንዳው ዩዌሪ ሙሴቪኒ ነጮች በአፍሪካ ላይ በመድኃኒት ጥቁሮችን እንዳይጨርሱ ያደረጋቸው ከብት አርቢ መሆናችን ነው፡፡ ብዙውን በሽታ ከብቶቹ ወስደውታል፡፡ ከከብት ጋር በመኖራችንም የመቋቋም ውሳጣዊ ዐቅም ገንብተናል ብለው ነበር፡፡] ልጆቻቸውን ለጉልበት ሥራ አስገድዶ በመውሰድ፣ እንዳይወልዱ የማምከኛ መድኃኒት በመስጠት፣ የመጠጥ ሱሰኞች ሆነው እንዲቀሩ በማድረግ አቦርጅኖች ከሀገር እንዲጠፉና ቁጥራቸው እንዲቀንስ ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት በሁለት መቶ ዓመታት ውስጥ እየጠፉ መጥተው በ1900 ዓም አካባቢ ቁጥራቸው ወደ 96 ሺ ወርዶ ነበር፡፡ አሁን ከጠቅላላው ሕዝብ 2 በመቶ ብቻ ናቸው፡፡ እሥር ቤት ስሄዱ ግን 25% እሥረኞች እነርሱ ሆነው ታገኛላችሁ፡፡ ልክ በአሜሪካ አፍሪካ አሜሪካውያን ከጠቅላላ ሕዝቡ 30 በመቶ ቢሆኑም እሥር ቤት ግን 60 ከመቶ እንደሆኑት ዓይነት ማለት ነው፡፡ 

አንዳንድ ጊዜ ለነጻነታችን ለተዋጉት አርበኞች ክብር የምትሰጡት ይህን መሰል የመከራ ታሪኮችን ስትሰሙ ነው፡፡ ‹በኋላ የመጣ ቀንድ በፊት የመጣን ጆሮ በለጠው› እንደተባለ በኋላ ሀገር የወሰዱት ዜጎች ክብሩንም፣ ነጻነቱንም፣ ኢኮኖሚውንም፣ ሥልጣኑንም ነጥቀውት ባላገሩን ሁለተኛ ዜጋ ሲያደርጉት ስታዩ ‹ነጻነት ሆይ ዋጋሽ ምን ያህል ነው?› ትላላችሁ፡፡ አንዳንድ ወገኖቼ ‹ጥቂት ቅኝ ብንገዛ ኖሮ እንሠለጥን ነበር፣ እናድግም ነበር› ብለው ይቆጫሉ፡፡ በእሳት የሚጫወት የአበራሽን ጠባሳ ያላየ ብቻ ነው፡፡ ባይሆን እኛ ‹ነጻነትን አላግባብ በመጠቀም ወንጀል›› ልንቀጣ የሚገባን ሕዝቦች ነን፡፡ ነጻነታችንን ለዕድገትና አንድነት፣ ለብልጽግናና ለመልካም አስተዳደር ከመጠቀም ይልቅ ለጦርነት ተጠቅመንበታል፡፡ የውጭ ወራሪዎችን ተከላክለን ራሳችን በራሳችን ስንዋረር ኖረናል፡፡ ነጻነትን ለጦርነት የመጠቀም ልማዱ አልለቀን ስላለም በአንጻራዊነት የመብት ነጻነት ተከብሮባቸዋል ወደሚባሉት ሀገሮች ስንገባ እንኳን ‹የዘሬን ያንዘርዝረኝ› ብለን ጦርነቱን ቀጥለነዋል፡፡ በሀገር ቤትም ሆነ በውጭው ዓለም ያሉ የፓርቲና የኮሙኒቲ፣ የሚዲያና የኪነ ጥበብ፣ የቤተ እምነትና የማኅበራዊ ተቋማት አደረጃጀቶቻችን ሁሉ የጦርነት አደረጃጀቶች ናቸው፡፡ የህልውናችን መሠረቱ ጠላት ነው፡፡፡ ያለ ጠላት ህልው መሆን ስለማንችል ጠላት ካጣን ጠላት እንፈጥራለን፡፡

‹እንግዳ ሆነሽ ትመጭ ባለቤት ሆነሽ ትቆጭ› እንደሚባለው በኋላ ዘመን የመጡትና ባለቤትነቱን የወሰዱት እንግሊዞች እነዚህን ነባር ሕዝቦች እንዳይድኑ አድርገው ሰብረዋቸዋል፡፡ ዛሬ ምንም እንኳን ችግሩ የተቀረፈ፣ መንግሥትም ለተፈጸመው ግፍ ይቅርታ የጠየቀ፣ እነርሱን የሚደግፍ ሕግም ያወጣ ቢሆን አካላዊ፣ ባህላዊና ሞራላዊ ህልውናቸውን እንዲያጡ በመደረጉ የተነሣ ወደ ጥንቱ ክብራቸው ለመመለስ አልቻሉም፡፡ እንግሊዞቹ እነዚህን ሕዝቦች ከምቹ የመኖርያ ሥፍራዎች በማስለቀቅ ወደ በረሃማውና ለኑሮ አስቸጋሪ ወደሆነው አካባቢ ገፍተዋቸዋል፡፡ ለብዙ ዘመናት ትምህርትና ሥልጣኔ እንዳይቋደሱ ተደርጓል፡፡ ከዚህ ይልቅ መጠጥና አደንዛዥ ዕጽ በአካባቢያቸው እንዲስፋፋ አድርገዋል፡፡ የቤተሰብን ማኅበራዊነት በመበተን ወላጆችና ልጆች እንዲለያዩ አድርገዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ ተደምረው ዛሬም የአውስትራልያ አቦርጅኖች በሀገራቸው ሙሉ በሙሉ የሚያዝዙ አልሆኑም፡፡

ከአውሮፓውያን መካከል አውስትራልያን ለመጀመሪያ ጊዜ የጎበኛት ሆላንዳዊው አሳሽ ዊልያም ጃንስዘን ነው፡፡ ዊልያምስ በሰሜን አውስትራልያ የረገጠውን መሬት ‹አዲሲቷ ሆላንድ› ብሎ ሰየመና የሀገሩ ግዛት አደረጋት፡፡ እርሱን ተከትሎ ወዲያው የመጣ አውሮፓዊ ሠፋሪ ግን አልነበረም፡፡ ከእርሱ በኋላ ዊልያም ዳምፐር የተባለ እንግሊዛዊ በሰሜናዊ ምዕራብ አውስትራልያ በ1688 ደረሰ፡፡ እንግሊዞች ወደ አውስትራልያ እግራቸውን መስደድ የጀመሩት ከዚያ ጊዜ በኋላ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ በ1770 ጄምስ ኩክ በተባለ መቶ አለቃ አማካይነት ወደ ምሥራቃዊው አውስትራልያ ክልል በመምጣት በእንግሊዙ ንጉሥ ጆርጅ ሦስተኛ ስም አካባቢውን ያዙና ‹ኒው ሳውዝ ዌልስ› ብለው ጠሩት፡፡

እንግሊዞች ወደ አውስትራልያ ፊታቸውን እንዲያቀኑ ያደረጓቸው ብዙ ምክንያቶች ነበሩ፡፡ በአንድ በኩል የአሜሪካ ግዛታቸው ነጻ መውጣት የእርሻ ቦታቸውን ነጥቋቸዋል፡፡ ስለዚህም ሌላ ቦታ በማፈላለግ ላይ ነበሩ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ወንጀለኞቻቸውን ያሥሩባት የነበረችው አሜሪካ ነጻ መውጣቷ ሌላ የወንጀለኞች ማሠሪያ እንዲያፈላልጉ አስገድዷቸው ነበር፡፡

እንግሊዞች ወታደሮቻቸውንና ወንጀለኞችን ይዘው በ1788 ዓም ወደ አውስትራልያ በመምጣት በሲድኒ በኩል አካባቢውን እያጸዱ መቆጣጠር ጀመሩ፡፡ በአሜሪካ የባሮችን ጉልበት ያጡት እንግሊዞች በአውስትራልያ የእሥረኞችን ጉልበት መጠቀም ጀመሩ፡፡ እየቆዩም ከተለያዩ ሀገሮች የመጡ ስደተኞች ተቀላቀሏቸው፡፡  

ዛሬ በአውስትራልያ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ ከ220 በላይ ሀገር ሰዎች ይኖሩባታል፡፡ ምንም እንኳን ዋናው ኦፊሴልዊ ቋንቋዋ እንግሊዝኛ ቢሆን ከ224 ቋንቋዎች በላይም ይነገሩባታል፡፡ የፌዴራል ሥርዓት የምትከተለው አውስትራልያ የሀገሪቱ ርእሰ ብሔር የእንግሊዟ ንግሥት ናት፡፡ (በነገራችን ላይ ንግሥቲቱ ካናዳን ጨምሮ የ16 ሀገሮች ርእሰ ብሔር ናት) የ2006 ዓም የሀገሪቱ የቆጠራ ውጤት እንደሚገልጠው ከሕዝቡ ቁጥር ሩብ ያህሉ ከተለያየ ሥፍራ መጥቶ የሚኖር ነው፡፡ ጣልያኖች፣ ቻይናዎች፣ ቬትናሞች፣ ሕንዶችና ፊሊፒኖች ከስደተኞቹ መካከል ከፍተኛውን ቁጥር ይይዛሉ፡፡ ከአፍሪካ አህጉር ብቻ ከ48 ሀገሮች የመጡ ስደተኛ ነዋሪዎች በአውስትራልያ ይገኛሉ፡፡

በ2006 ዓም የተደረገው የአውስትራልያ ሕዝብ ቆጠራ በሀገሪቱ 7516 ኢትዮጵያውያን እንደሚኖሩ ይገልጣል፡፡ ነባር ነዋሪ ኢትዮጵያውያን ግን ቁጥሩን የዚህ ሦስት እጥፍ አካባቢ ያደርጉታል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ለቆጠራው ቅጽ ትኩረት ባለመስጠታቸው እንደማይሞሉት፣ አንዳንዶቹም የቋንቋው ችግር ሳይረዱት እንዲቀሩ እንደሚያደርጋቸው፣ ሌሎቹም ከቆጠራው በኋላ በብዛት መምጣታቸውን እንደ ምክንያት በመውሰድ የኢትዮጵያዊውን ቁጥር እስከ ሃያ ሺ ያደርሱታል፡፡ የአውስትራልያ መንግሥት ቆጠራ እንደሚያሳየው 26 በመቶዎቹ የሀገሬ ልጆች በሹፍርናና ማሽኖችን በማንቀሳቀስ፣ 24.3 በመቶዎቹ በጉልበት ሥራ፣ 16.3 በመቶዎቹ በአገልግሎት ዘርፍ፣ 33.5 በመቶዎቹ ደግሞ በአስተዳደር፣ በጸሐፊነት፣ በቴክኒክ ሥራ፣ እንዲሁም በሌላ ሞያ ነክ ሥራ መሠማራታቸውን ያሳያል፡፡ በሀገሪቱ ከሚኖሩት ኢትዮጵያውያን መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት እዚህ እኔ ያለሁበት ቪክቶርያ ግዛት፣ ሜልበርን ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ናቸው፡፡

አዳሙ ተፈራ ‹ገመናችን በሰው ሀገር› ብለው በጻፉት መጽሐፍ ላይ እንደገለጡት ወደ አውስትራልያ ለመጀመሪያ ጊዜ የገቡት ኢትዮጵያዊ አቶ አዲስ ታምሩ ይባላሉ፡፡ እኒህ በ1965 ዓም ወደ አውስትራልያ የገቡት የኢትዮጵያ አየር ኃይል ባልደረባ ለትምህርት መጥተው ነው በዚሁ የቀሩት፡፡ ዛሬ ከሀገሩ ነባር ነዋሪ (አቦርጅን) ጋር ተጋብተው ይኖራሉ፡፡

እዚህ የሚኖሩ የሀገሬ ልጆች ብዙ አስገራሚ፣ ብዙ አስቂኝ፣ ብዙም አሳዛኝ ገጠመኝ አላቸው፡፡ እድሜና ጤና ከሰጠን አብረናቸው እናዝናለን፣ እንስቃለን፣ እንሳቀቃለንም፡፡

ሜልበርን፣ አውስትራልያ

ባለፈው ሳምንት በቡሩኖ ደሴት በምትገኘው ብሩናይ አውሮፕላን ማረፊያ ነበር የተለያየነው፡፡ አንዲት የሀገሬን ሰዎች የመሰለች ልጅ ወደ እኔ አቅጣጫ ስትመጣ አይቼ፡፡ ልጅቱ መጣች፡፡ እንደ ዓይኔ ምስክርነት ከሆነ የሀገሬ ልጅ ናት፡፡ በአንገቷ ላይ ጣል ያደረገችው ሻርፕ ነገርም ነጠላ ቢጤ ነው፡፡ እንዲያውም የሆነ ጥልፍ ነገር ይታየኛል፡፡ መጣችና ከእኔ በትይዩ ከሚገኘው የተደረደረ ወንበር መካከል ተቀመጠች፡፡ ይኼኔ ዓይኔን ተጠራጠርኩት፡፡ ኢትዮጵያዊት አይደለችም ማለት ነው? አልኩ በልቤ፡፡ መሆን አለመሆኗን ለማረጋገገጥ የሆነ ምልክት መፈለግ ጀመርኩ፡፡ ምንም ነገር ሳጣ ‹‹ለምን አልጠይቃትም›› አልኩና አመራሁ፡፡

ወደ ወንበሯ ስጠጋ ባደረገችው ሻርፕ ላይ ኦዳ (የኦሮሞ ባሕላዊ መለያ የሆነው ዋርካ) ተጠልፎ አየሁት፡፡ በዚህ ተጽናናሁና

‹‹ኢትዮጵያዊት ነሽ›› አልኳት በአማርኛ፡፡

‹‹ይቅርታ አይደለሁም›› አለችኝ በእንግሊዝኛ፡፡

‹‹ይህንን የልብሱን ጌጥ ግን ዐውቀዋለሁ›› አልኳት እኔም በእንግልጣር፡፡

ቀና ብላ በአግራሞት እያየችኝ ‹‹ልክ ነህ ኦዳ ነው›› አለችኝ፡፡

‹‹ታድያ ቢያንስ በትውልድ ኢትዮጵያዊ ነሻ›› አልኳት እንደ ቀልድ፡፡

‹‹አይደለሁም›› ብላኝ ኮስተር አለች፡፡

እንዲህ ዓይነት ነገር በአሜሪካ ሚነሶታ አጋጥሞኝ ስለሚያውቅ ተጠራጠርኩና በእንግሊዝኛ ‹‹ይቅርታና ታድያ የየት ሀገር ሰው ነሽ?›› አልኳት፡፡

አሁን ከእርሷ አለፍ ብየ ቁጭ ብያለሁ፡፡ ‹‹እኔ ከኦሮሚያ ነኝ›› አለችኝ፡፡ ስልኳን እየነካካች፡፡

‹‹እኔምኮ ከኦሮሚያ ነኝ፡፡ አዲስ አበባ የኦሮሚያ ዋና ከተማ አይደለች እንዴ›› አልኩ ለቀልድ ያህል፡፡

‹‹አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ናት፤ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ፊንፊኔ ናት፡፡ አሁን እኔና አንተ መነጋገሩ ምን ይፈይድልናል›› አለች ለመገላገል ብላ፡፡

‹‹እኔና አንቺ ካልተነጋገርንማ ማንና ማን ተነጋግሮ መፍትሔ ያመጣል ታድያ››

‹‹ምናልባት ላንግባባ ስለምንችል››

‹‹አለመግባባታችንን በምን ዐወቅሽው?››

ተመቻቸችና ‹‹ለምሳሌ እኔ ፊንፊኔ ስል አንተ አዲስ አበባ አልክ፣ ለእኔ ኦሮሚያ ቅኝ የሚገዛ ሀገር ነው፤ ላንተ ደግሞ ክልል ነው፤ ታድያ እንዴት እንግባባለን?››

‹‹ሰዎች ሊግባቡ የማይችሉትኮ የተለያዩ ሃሳቦችን ስለሚይዙ አይደለም፡፡ የተለያዩ ሃሳቦቻቸውን የማስማሚያ መንገድ ስለማይኖራቸው ነው፡፡ ደግሞም የግድኮ መግባባት አይጠበቅብንም፤ ቢያንስ እንገናዘባለን፡፡ አሁን አንቺ ፊንፊኔ አልሽ፣ እኔ አዲስ አበባ አልኩ፤ ምናልባትም ከአዲስ አበባና ከፊንፊኔ በፊትም ቦታው ሌላ ስም ሊኖረው ይችላል፡፡ አዲስ አበባ ከየቦታው በግድም በውድም የመጣን የሀገሬው ሰዎች ብቻ ሳንሆን ጣልያኖችም፣ ግሪኮችም፣ ዐረቦችም፣ አርመኖችም፣ እንግሊዞችም፣ ፈረንሳዮችም፣ ሌሎችም ባዋጣነው አስተዋጽዖ እዚህ ደርሳለች፡፡ እንዲያውም በሌላው ሀገር እንዲህ የብዙ ዓይነት ወገን አሻራ ያረፈባት ከተማ ስትገኝ እንደ ልዩ ነው የምትታየው፡፡ የሚፈለገውም የሁሉ እንድትሆንና ሁሉም አስተዋጽዖውን የእኔ ብሎ እንዲቀጥል ነው፡፡ ቻይና ታውን፣ ኢትዮጵያን ስትሪት፣ ኮርያ ሠፈር፣ ስፓኒሽ ጎዳና እያሉ ለአስተዋጽዖ አድራጊዎቹ ዕውቅና በመስጠት የሁሉ እንድትሆን ያደርጓታል፡፡ አዲስ አበባ ወይም ፊንፊኔም እንዲሁ ናት፡፡

‹‹በሕዝብ ፍልሰትና በጦርነት በኖረ ሀገር የስም ተፋልሶ ያለ ነገር ነው፡፡ ለምሳሌ በምዕራብ ሸዋ ‹ወረብ›ና ‹እንደገብጦን› የሚባሉ የጋፋቶች ግዛቶች ነበሩ፤ በኋላ ግን በኦሮምኛ ስሞች ተተክተዋል፡፡ በምሥራቅ ሸዋ እነ ፈጠጋር፣ እነ ወጅ፣ እነ መሐግል ስማቸውን አጥተው ቀርተዋል፡፡ ዛሬ የመተሐራ አካባ የሚባለው ጥንት መሐግል ነበረ፡፡ ጎጃም ብትሄጂ አቸፈር፣ ሜጫ፣ አዴት፣ ዴንሳ፣ ብቸና የኦሮሞኛና የኦሮሞኛ ነክ ስሞች ናቸው፡፡ በፊት ግን የአገውና የአማራ ስሞች ነበሩባቸው፡፡ ያ ማለት ግን ቅኝ ተገዝተዋል ማለት አይመስለኝም፡፡

‹‹በባሌ፣ በሐርና በሸዋ ብዙ የአርጎባ ስሞች ወደ ኦሮምኛ ተቀይረዋል፡፡ በወለጋና በደቡብ ሸዋ ሰባቱ የጋፋት ፌዴሬሽን አካላት ይገኙባቸው የነበሩ ቦታች ዛሬ ሰዎቹም ስማቸውም ጠፍቶ ቀርቷል፡፡ ስማቸው ብቻ አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ የጥበበ ዕድ ኢንዱስትሪ ታላቅ ቦታ የነበራቸው፣ በሕክምናና አስተዳደር ችሎታቸው የተመሰከረላቸው ጋፋቶች በኦሮሞ ፍልሰት ጊዜ ከመካከልና ከደቡብ የሀገራችን ክፍሎች ወጥተው መጀመሪያ ወደ ጎጃም ተሻገሩ፤ ከዚያም ደግሞ ቀስ በቀስ እየተዋጡ ጠፉ፡፡ ዛሬ ቋንቋቸውም ሆነ ባህላቸው ከኦሮሞዎች፣ ከአማሮችና ከአገዎች ጋር ተዋሕዶ ሕልውናውን አጥቷል፡፡

‹‹በትግራይ፣ በወሎና በጎጃም የአገው ሕዝቦች ከጥንት ጀምሮ ተስፋፍተውባቸው የነበሩ ቦታዎች በአማራና በትግራይ ሕዝብ ተውጠው፣ ስማቸውንም ቀይረው ጠፍተዋል፡፡ በደቡብ ምዕራብ ትግራይ የነበሩት የዶባ ሕዝቦች በአፋርና በትግራይ ተውጠው የቦታዎቻቸው ስሞችም ተቀይረው፣ ከጥቂቶች በቀር ጠፍተዋል፡፡ የጥንቷ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ተብለው የተመዘገቡትኮ አሁን ስማቸውን እንኳን አንሰማውም፡፡ ምናልባት ከአገው ሕዝቦች በቀር፡፡ ክርስቲያን ቶፖግራፊ በተሰኘው የኮስሞስ መጽሐፍ ውስጥ በአዱሊስ ያገኘውን የካሌብ የድንጋይ ጽሑፍ አኑሮልናል፡፡ በዚያን ጊዜዋ ኢትዮጵያ የተገለጡት ሕዝቦች ጋዜ፣ አጋሜ፣ ሲጊን፣ አቫ፣ ዚጋሪን፣ አጋቬ፣ ቲያማ፣ አታጋውስ(አገዎች)፣ ካላ፣ ሰሜን፣ ላዚን፣ ዚአ፣ ጋቫላ፣ አታልሞ፣ ቤጃ፣ ›› የሚባሉ ሕዝቦች ናቸው፡፡ ብዙዎቻችን እዚህ ዝርዝር ውስጥ የለንም፡፡ እነዚህ ቦታዎች ግን ዛሬ ወይ የወንዝ፣ ወይ የጎጥ፣ ወይ የተራራ ስሞች ሆነው ቀርተዋል፤ ያለበለዚያም ተለውጠዋል፡፡ ወሎ ብትሄጂ የአማራው ዋና ቦታ የነበረው ወለቃ ዛሬ ስሙ ቦረና ተብሏል፡፡ ወለቃ የወንዙ ስም ሆኖ ቀርቷል፡፡›› ስልኳን እየነካካችም ቢሆን ስትሰማኝ ቆየችና

‹‹የኦሮሞ ሕዝብ ግን የተለየ ነው፤ የሀገሪቱን ሰፊ ክፍል ይዞ ከሀገሪቱ ተጠቃሚ ሳይሆን፤ መሬቱንና መብቱን ተቀምቶ በገዛ መሬቱ ለሌሎች ገባር ሆኖ፤ ቋንቋውና ባህሉ ተረግጦ፤ ሌሎች ሕዝቦች መጥተው አገሩን ወስደውበት የሚኖር ሕዝብ ነው፡፡ በግድኮ ነው ኢትዮጵያ የሆነው፤ ኢትዮጵያ የሰሜን ሕዘቦች እንጂ የደቡቦቹ መጠሪያ አይደለችም፡፡ ኢትዮጵያ ሌላውን ጠቅልላ ነው የያዘችው፡፡›› አለችኝ፡፡ መነጋገሩን ወዳዋለች ማለት ነው፡፡

‹‹እይውልሽ እኅቴ እኔኮ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ ምንም ነገር አልደረሰም፤ መብቱ አልተነካም፣ መከራ አልተቀበለም፤ አልተሰቃየም፤ መሬቱን አልተነጠቀም፤ ሌሎች መሬቱን አልወሰዱበትም አይደለም የምልሽ፤ ነገር ግን ይህ ነገር የብዛትና ማነስ ካልሆነ በቀር በሁሉም ላይ የመጣ ነው፡፡ በዚያች ሀገር ውስጥ ለሥልጣንና ለሀብት ብዙ ትግግሎች ተደርገዋል፡፡ ‹‹ወረራ››፣ ፍልሰት፣ ጦርነት፣ ንጥቂያ፣ ስደት ተከስቷል፡፡ ይህ ግን የአንድ ሕዝብ ብቻ ስቃይ መገለጫ አይደለም፡፡ የብዛትና ማነስ ካልሆነ የሁላችንም አያቶች ቀምሰውታል፡፡ ጎንደሬው ዐፄ ቴዎድሮስኮ ጎንደሬዎቹን እጃቸውን ቆርጠዋል፣ በአንድ ቤት ውስጥ አስገብተው አቃጥለዋቸዋል፡፡ እንዲያውም ኦሮሞውን ምንም አላደረጉትም፡፡ ያ ግን የሥልጣን ጥያቄ እንጂ በአንድ ዘር ላይ የተፈጸመ ወንጀል አይደለም፡፡ ሁላችንም የያዝነው የተፈጠርንበትን መሬት ብቻ አይደለምኮ፡፡ ኦሮሞውም ቢሆን ከአማራው፣ ከትግሬው፣ ከጋፋቱ፣ ከአርጎባው፣ ከጉራጌው፣ ከሲዳማው፣ ከሌሎች ከጠፉ ሕዝቦች መሬት ወስዷል፡፡ ሁላችንም እዚህ አይደለም የነበርነው፤ አስፍተን ይዘናል፤ ተገፍተን ለቅቀናል፤ ተውጠን ቀርተናል፤ ውጠን ተዋሕደናል፡፡ የነገሥታቱን ታሪክ ስናይኮ የኦሮሞውም ሕዝብ ወደ ሸዋ፣ ወደ ጎጃም፣ ወደ ጎንደርም እየዘለቀ ከብት ዘርፏል፤ ሰዎች ገድሏል፤ እህል አቃጥሏል፡፡ መሬት ወስዷል፡፡ በጎጃምና በወለጋ ኦሮሞዎች ዘንድ ዓባይን እያለፉ የመዘራረፍ፣ የመገዳደል፣ የመዋጋት፣ ከዚያም በላይ የመጋባት ታሪክ ነበርኮ፡፡ ይህኮ ለኢትዮጵያ አዲስ አይደለም፡፡ ሁላችን እንዲህ ሆነን ነው እየተፈጠርን የመጣነው፡፡ ደግሞም ‹የመርገምት በረከት› እንደሚባለው ይህ ነገር አዋሕዶ ፈጥሮናል፡፡

‹‹የነበረው ትግልኮ ሀብትና ሥልጣንን መሠረት ያደረገ እንደነበር የምታዪው አንድ ‹ዘር› የሚባሉትም እርስ በርሳቸው ሀብትንና ሥልጣንን ለመንጠቅ ሲሉ ሲዋጉ መኖራቸው ነው፡፡ ዐፄ ቴዎድሮስ ጎጃም ገብተው ብዙ ሕዝብ ጨርሰዋል፡፡ ሞጣ አካባቢ ብትሄጂ የሚዘገንን ታሪክ ይነግሩሻል፡፡ ሸዋ ወርደው ብዙ እጆች ቆርጠዋል፡፡

ዐፄ ቴዎድሮስ እጅግ ተዋረዱ

የሸዋን ሰው ሁሉ እጅ ነሥተው ሄዱ የተባለውን አልሰማሽ፡፡

ያንን ግን አማራውን ከመጨቆንና ከማጥፋት አንጻር ካየነው፣ ቅኝ ግዛት አድርገን ከተመለከትነው ስሕተት ይመስለኛል፡፡ ሰዎች ተጨቁነዋል፤ አዎ፡፡ በራስ ሚካኤል ጊዜ ወሎና ሸዋ ተዋግቷል፡፡ በምኒሊክና በተክለ ሃይማኖት ምክንያት እምባቦ ላይ ሸዋና ጎጃም ተጫርሷል፡፡ ዐፄ ሱስንዮስ ከሸዋ አስከትለዋቸው ለሄዱት የኦሮሞ ወታደሮች የጎንደርን መሬት ከየአድባራቱ እየቀሙ እንዳደሏቸው የማኅደረ ማርያም ታሪክ በዝርዝር ይነግረናል፡፡ አንዱ ከካህናቱ ጋር ያጣላቸውም ይኼው ነበር፡፡

ዐፄ ታዎፍሎስ (1701-11) በነገሡ በሦስተኛው ዓመት ኦሮሞዎች ወሎ አምሐራ ሳይንት ወደምትገኘው አትሮንሰ ማርያም ደብር ገብተው በሮቿን ሰበሩ፤ ካህናቱንም በሙሉ ገደሉ፡፡ ምእመናኑንም ሁሉ ማረኩ፤ ዐፄ በዕደ ማርያም በፈረንጅ እጅ ያሳለውን የእመቤታችንን ሥዕልና የዐፄ በዕደ ማርያምን ዐፅም ሁሉ ነሐሴ 9 ቀን አውጥተው መሬት ለይ ጣሉት›› ይላል ዜና መዋዕሉ፡፡ እንግዲህ ይህንን ስታዪ እዚህች ሀገር ሳያጠፋም ሳይጠፋም የኖረ ሕዝብ አለመኖሩን ነው የምታዪው፡፡ ይህ ግን ኦሮሞዎች የኦርቶዶክስን እምነት ለማጥፋት፣ ወይም አማሮችን ለማጥፋት ብለው ያደረጉት አይመስለኝም፡፡ የሀብትና የሥልጣን ትግል ነው፡፡

ደግሞም በአንድ አካባቢ በነበረ ስም ተጠቅልሎ መጠራት በኛ አልተጀመረምኮ፡፡ ሀገር ተቀናንሶ ያንሳል፤ ወይም እምብርቱን ይዞ እየሰፋ ይሄዳል፡፡ አፍሪካ የሚለው ስም ላቲኖች በዛሬዋ ቱኒዚያ ለነበሩት ካርታጎአውያን የሰጡት ስም ነበረ፡፡ በመጀመሪያ አካባቢ የሊቢያ ጎሳዎችን ለመጥራት ነበር የሚውለው፤ በበርበሮች ቋንቋ ‹ኢፍሪ; ማለት ‹ዋሻ› ማለት ሲሆን ‹‹በዋሻ የሚኖሩ›› ለማለት የተጠቀሙበት ነው፡፡ ላቲኖች ‹ኢፍሪ› በሚለው ላይ ‹ኢካ› የሚለውን ለቦታ የሚቀጠል ቅጥያ ቀጠሉበትና ‹አፍሪካ› ብለው ጠሩት፡፡ በኋላ ግን የሁላችንም መጠሪያ ሆነ፡፡ እስያ ጥንት ዛሬ ቱርክ የያዘችው ቦታ መጠርያ ነበር፡፡ ዛሬ ግን እንዲያውም የሚጠሩበት የሩቅ ምሥራቅ ሕዝቦች ናቸው፡፡

‹‹አየህ›› አለችኝ መነጽሯን አስተካክላ፡፡ ‹‹አየህ አንተ ጭቆናው አይሰማህም፤ ምክንያቱም ከተጨቆኑት ወገን አይደለህምና፡፡ የደረሰብህ ነገር የለም፤ የመከራውን ገፈት አልቀመስከውም፡፡ እንደኛ በገዛ ሀገርህና መሬትህ ግፍ ቢደርስብህ፣ እንደኛ ቅኝ ተገዝተህ የቅኝ ግዛትን መራራ ነገር ብትቀምሰው እንደዚህ አትልም ነበር፡፡ አንዱ ልዩነታችን ከዚህ የሚመጣ ነው፡፡ በተግባር በቀመሰውና በትምህርት በሚያውቀው መካከል የሚኖር ልዩነት››

‹‹አንቺምኮ ከሌሎች ሰማሽው፣ አነበብሽው ወይም ወረስሽው እንጂ አልደረሰብሽም፡፡ የደረሰና የሚደርስ ካለም በሁሉም ላይ ይደርስ ይሆናል እንጂ የተለየ ነገር አሁን አይደርስብሽም፡፡

‹‹ለምሳሌ በስድሳ ስድስት አብዮት ጊዜ በአብዛኛው በቀይ ሽብር ያለቁት ኦሮሞዎች ናቸው›› አለች ስልኩን ወንበሩ ላይ አስቀምጣ፡፡

‹‹በምን ታወቀ?››

‹‹መረጃዎች አሉ››

‹‹ማን ነው ያን ጊዜ ሬሳ እያገላበጠ ዘር እየቆጠረ መረጃ የሰበሰበው››

‹‹ቢያንስ አብዛኛው የሀገሪቱ ሕዝብ ኦሮሞ በመሆኑ በብዛት የሚሞተው እርሱ ነው››

‹‹እንዴ አንድ ሕዝብኮ በብዛት ይኖራል ማለት በብዛት ይሞታል ማለት አይደለም፡፡ በወቅቱ በነበረው ተሳትፎ ነው የሚወሰነው፡፡ ያኔኮ የመፈረጃው ሳጥን ፀረ አብዮት፣ ፀረ ሕዝብ፣ አድኃሪ፣ ቡርዡዋ፣ ኢሕአፓ፣ ምናምን የሚል ነው፡፡ የዘር ፍረጃ አልነበረውም፡፡ አንዳንዴ ችግሩ እኔ ብቻ ነኝ መከራ ያየሁትና እኔ ብቻ ነኝ መፍትሔ የሚያስፈልገኝ ከሚል የሚመጣም ይመስለኛል፡፡ ችግሮችን ለመፍታት መነሣት እንጂ የተወሰኑ አካላትን ከችግር ለማላቀቅ መነሣት ተመልሶ ባልተፈቱት ችግሮች ወጥመድ የሚጥል ነው፡፡››

‹‹ከሆነ አካባቢ ነገሥታቱ መነሣታቸው በዓለም ታሪክ የተለመደ ነው፡፡ እንደ ፓርላማ ሥርዓት ንጉሣዊ አስተዳደር ሁሉን ያማከለ ሊሆን አይችልም፡፡ ኖርዌይን ሲገዟት የኖሩት የዴንማርክ ንጉሣውያን ቤተሰቦች ናቸው፡፡ አሁንም በእንግሊዝ ንጉሣዊነት በዘር ግንድ የሚሄድ ነው፡፡ አሁንም በጃፓንና ስፔን እንዲሁ ነው፡፡ በእሥራኤልም ታሪክ ብናየው የይሁዳ ቤት ነው፡፡ ይኼኮ የሰው ልጅ በሆነ ዘመን የደረሰበት ደረጃ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከዚያ የተለየች አትሆንም፡፡

‹‹ነገሥታቱ ከአማራው ወገን ስለነበሩኮ በ66 አብዮት የአማራው ሕዝብ አጥር ሆኖ ከውድቀት አላዳናቸውም፡፡ ንጉሣዊው ሥርዓት ሲወድቅኮ በተማሪው ንቅናቄ፣ በወታደሩ፣ በፓርቲዎች፣ በሠራተኛ ማኅበሩ ውስጥ የተለያዩ ማኅበረሰቦች ናቸው የነበሩት፡፡ ጨቁነውናል ብለው ከተነሡት ሕዝቦች መካከልኮ አማሮችም፣ ትግሬዎችም፣ ኦሮሞዎችም፣ ሲዳማዎችም፣ ወላይታዎችም፣ ጉራጌዎችም፣ ሶማሌዎችም ነበሩበት፡፡ እንዲያ ባይሆን ኖሮማ ተጠቅመናል በሚሉት አማሮችና ተጨቁነናል በሚሉት ሌሎች መካከል የርስ በርስ ጦርነት ይነሣ ነበር፡፡ አሁንኮ ያለፈውን ታሪክ በግልጥ መነጋገር፣ ከዚያ ትምህርት መውሰድና እንዳይደገም ማድረግ ነው የሚሻለው፡፡ እኛ ስለ ትናንት ብቻ ስንከራከር፣ ስለ ነገም ሳንነጋገር ስንት መልካም አጋጣሚዎች በዚህች ሀገር አለፉ፡፡ ስለ ትናንት ታግለን አብዮት እናመጣለን፤ ለውጥ ሲመጣ ግን ለነገ ያዘጋጀነው የጋራ የመግባቢያ ሰነድ ስለሌለን እንደገና አዙሪት ውስጥ እንወድቃለን፡፡ ተባብረን መሸከም ያልቻልነውን ችግር ለየብቻ እንሸከመዋለን ብሎ መመኘት ቅዠት ነው የሚመስለኝ፡፡››

ደኅና ሞቅ ወዳለው ውይይት በመግባት ላይ ሳለን

‹‹ወደ ማኒላ የምትሄዱ መንገደኞች ወደ በሩ ግቡ›› የሚል ማስታወቂያ ተነገረ፡፡ ቦርሳዋን ሸክፋ ከመቀመጫዋ ተነሣች፡፡

‹‹ደስ የሚል ቆይታ ነበር፡፡ እኔ ወደ ፊሊፒን ነው የምሄደው፤ የምኖረውም እዚያ ነው፡፡ በፊት ደቡብ አፍሪካ ነበርኩ፡፡ አሁን ወደ ሰባት ዓመት ሆነኝ፡፡ እዚያ ከመጣህ እንገናኛለን›› አለችኝ፡፡ የኢሜይል አድራሻየን ሰጠኋት፡፡ ወደ በሩ ስትገባ ዘወር ብላ ሰላም አለችኝ፡፡ አንደበቷ እንጅ ነፍስያዋ የሀገሬ ልጅ መሆንዋን ይነግራታልኮ፡፡

እኔም ከጥቂት ደቂቃዎች ወደ አውሮፕላኔ ገባሁ፡፡ ወደ አውስትራልያ ለመድረስ የሰባት ሰዓት በረራ ይጠብቀኛል፡፡ በቸር ሜልበርን ላይ እንገናኝ፡፡

ከብሩናይ ወደ አውስትራልያ መንገድ

ክርስትናን እሳት የሚያሸንፈው ቢሆን ኖሮ ድምጥያኖስና ዲዮቅልጥያኖስ በተሳካላቸው ነበር፡፡ ክርስትናን መግደል የሚያሸንፈው ቢሆን ኖሮ አይሁድና ሮማውያን፣ ኮሙኒስቶችና ማኦኢስቶች ድል በነሡት ነበር፡፡ ክርስትና በቤተ ክርስቲያኖች መቃጠል፣ በቅዱሳት መጻሕፍትም መቆነጻጸል የሚያበቃለት ቢሆን ኖሮ ኔሮንና ትራጃን፤ ዮዲት ጉዲትና ግራኝ ባስቆሙት ነበር፡፡ ክርስትና እሳት ሆኖ በእሳት ውስጥ ማለፍ ነው፡፡ ክርስትና እሳትን እሳት ሆኖ ድል መንሣት ነው፡፡ እዚህ እሳት ላይ ሦስቱ ሕጻናት ተጥለው ነበር፣ እዚህ እሳት ውስጥ ቂርቆስና እየሉጣ ተወርውረው ነበር፡፡ ይኼ እሳት ቅዱስ ፖሊካርፐስን በልቶት ነበር፡፡ ክርስትና ግን ይኼው አለ፡፡

ሊያጠፉት የተነሡት ሁሉ ተረት ሆነዋል፡፡ ክርስትና ግን ህያው ሆኖ አለ፡፡ የሠራነውን ቤተ ክርስቲያን ያቃጥሉ ይሆናል፣ የሠራነውን ሰማያዊ ቤት ግን አይደርሱበትም፡፡ ንብረታችንን ይወስዳሉ፣ እምነታችንን አያገኙትም፤ እኛን ይገድላሉ፤ ነፍሳችን ግን ከዐቅማቸው በላይ ናት፡፡ ይህንን መከራ አስቀድመን የማናውቀው ቢሆን ኖሮ በደነገጥን ነበር፡፡ ነገር ግን ክርስቲያን ስንሆን ይህ እንደሚመጣ እናውቅ ነበር፡፡ ‹ተዘጋጅታችሁ ተቀመጡ› ተብለናልና ተዘጋጅተን ነበር፡፡ እኛ ቆንጨራና ቦንብ፣ መትረጊስና አዳፍኔ አንይዝም፡፡ እኛ በጠጠር ጎልያድን የሚረታውን ይዘናል፡፡ በጩኸት ሳይሆን በዝምታ ኢያሪኮን የሚንደውን ይዘናል፡፡ በሁካታ ሳይሆን በርጋታ የሚሠራውን ይዘናል፡፡ እነርሱ ሲጮኹ ከአጋንንት ጋር ያወካሉ፤ እኛ ግን ዝም ስንል ከፈጣሪያችን ጋር እንነጋገራልን፡፡ ዛሬ በምድር ላይ የለኮሱትን እሳት ብዙዎች በሰማይ እነርሱው ይቀበሉታል፡፡

አይቀርም፤ አምላካችንም ዝም አይልም፡፡ እንገደላለን፤ ግን እናሸንፋለን፤ እንቃጠላለን፤ ግን እንለመልማለን፡፡ እናጣለን፤ ግን እናገኛለን፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከተቃጠሉት ሕንጻዎቿ በላይ ናትና፡፡

ግብጽ ከድጡ ወደ ማጡ እየተጓዘች ነው፡፡ ሀገርን ማናጋትና ማፍረስ ምንኛ ቀላል እንደሆነ እየተማርንም ነው፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የአስተሳሰብ፣ የበሰለ አመራር፣ የዴሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታና ብስለት፣ የታመነና የበሰለ ሚዲያ፣ መብቱንና ግዳጁን የተረዳና የሚወጣ ማኅበረሰብ፣ ልካቸውንና መልካቸውን የሚያውቁ የፍትሕ፣ የጸጥታና የውትድርና ተቋማት አጠቃላይ ውጤት እንጂ የምርጫ ሂደትና ውጤት ብቻ እንዳልሆነም እየተማርን ነው፡፡

የእሥራኤልና ፍልስጥኤምን የሰላም ድርድር አስመልክቶ በቅርቡ የተጠየቁት የእሥራኤል ፕሬዚዳንት ሺሞን ፔሬዝ ‹‹ድርድር ማለት እኛ መፍትሔ ነው ብለን የምናስበውን ለሌላ ለማሳመን የምናደርገው ውይይት አይደለም፤ ድርድር ማለት ሁለታችንም በጋራ የምንፈልገው ሌላ ሦስተኛ መፍትሔ ነው፡፡›› ብለው ነበር፡፡ ሌላ ሦስተኛ መፍትሔ ከመፈለግ ይልቅ ‹እንትን ወይም ሞት‹ ብለው የተሰለፉ የግብጽ ልጆች ሀገራቸውን ወደ ማትወጣበት ኪሣራ እየተከተቷት ነው፡፡

አንድ ‹ተረት  በሥዕል› የሚባል መጽሐፍ ውስጥ እንዲህ የሚል ማንበቤን አስታውሳለሁ፡፡ ሁለት ውሾች መንገድ ላይ ሲሄዱ ከሥጋ ቤት መኪና የወደቀ ምርጥ ሥጋ ያያሉ፡፡ ሁለቱም ወደ ሥጋው ይፈተለካሉ፡፡ ሁለቱም ግን ሥጋው ጋ ከመድረሳቸው በፊት ይፋጠጣሉ፡፡ ሥጋውን እኔ ብቻ ነኝ መብላት ያለብኝ በሚል አባዜ ውስጥ ገብተው ከሥጋው ጎን መናከስ ጀመሩ፡፡ በእግር እየተገፋፋ፣በጥርስ እየተቧጨቁ ቀኑን ሙሉ ሲናከሱ ዋሉ፡፡ በመጨረሻም ተዳከሙ፡፡ ደማቸው ፈስሶ፣ ቆዳቸውም ተሰነጣጥቆ ምድር ላይ ተዝለፍልፈው ወደቁ፡፡

በዚህ መካከል እንዲት ቀን የሰጣት ቡችላ መጣች፡፡ ስታይ ሁለት ደቦል የሚያክሉ ውሾች መሬት ላይ ተጋድመው ያቃስታሉ፡፡ ከአጠገባቸውም ምን የመሰለ ጮማ ሥጋ ተጋድሟል፡፡ ብታያቸው ካሉበት የሚንቀሳቀሱ ዓይነት አይደሉም፡፡ መጀመሪያ ወደ ሥጋው ጠጋ አለች፡፡ በድካም ተገላብጦ ከማየት በቀር ለማስጣል ዐቅም ያለው አልነበረም፡፡ ሥጋውን መንጨት ስትጀምር ከሚያቃስት ድምጽ በቀር የከለከላት የለም፡፡ በመጨረሻም እየጎተተች ወሰደችው፡፡

ቀማኛ ሲጣላ

ተስማምቶ እንዳይበላ

መንትፋቸው ሄደች ዘዴኛ ቡችላ

የሚል በተረቱ መጨረሻ ላይ ሠፍሯል፡፡

በአብዮቱ ዘመን ልሂቃኑ መግባባት፣ ከሚከተሉት ርእዮተ ዓለም ውጭም ሌላ ሦስተኛ መፍትሔ ማምጣት አቅቷቸው እርስ በርሳቸው ሲባሉና ሲናከሱ ሀገሪቱን ለወታደራዊው ጁንታ አስረከቧት፡፡ በተግባቦትና በውይይት፣ በዕውቀትና በልምድ እንዴት መፍትሔ እንደሚመጣ ከመሥራት ይልቅ ከማርክስና ሌኒን፣ ከማኦና ከኤንግልስ መጻሕፍት ውስጥ መፍትሔውን ሲፈልጉ በጠመንጃው መፍትሔ አመጣለሁ ለሚለው ደርግ ሁሉንም አስረከቡት፡

አብዛኞቹ የግብጽ የፖለቲካ ኃይሎች ሙባረክን ሕዝቡ ሲያነቃንቀው የተደራጁ ናቸው፡፡ የተግባባ ኃልይ፣ አቋም ያለው አባል፣ የተዘረጋ መዋቅር፣ የተጠና ፕሮግራም፣ በሕዝቡ ልብ ውስጥ የገባ ሃሳብ አልነበራቸውም፡፡ የሙስሊም ወንድማማቾች ግን ይህንን በበጎውም በክፉውም ዘመን ሲሠራ ነው የኖረው፡፡ ሀገሪቱ ወደ ምርጫ ስትሄድ የአንዳንድ ፓርቲዎች ሰዎች የተማሩ፣ የታወቁ፣ የተከበሩ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሠሩ ስለሆኑ ብቻ ሕዝብ ይመርጠናል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡ የተደራጀ ኃይል፣ የተዘጋጀ መዋቅር፣ የተግባባ አባል ግን አልነበራቸውም፡፡ አንዳንዶቹም ከፓርቲያቸው በላይ ሰዎቹ የገዘፉ ነበሩ፡፡ ፓርቲዎቻቸውም የሚጠሩት በፓርቲያቸው ስም ሳይሆን የእገሌ ፓርቲ እየተባሉ ነበር፡፡ ምርጫው ሲመጣ በሚገባ የሠራውና የተደራጀው የሙስሊም ወንድማማቾች ፓርቲ አሸነፈ፡፡ ልሂቃኑም ሀገሪቱን አሳልፈው ሰጧት፡፡ ይኼው ዛሬ የመውጫ መንገዱ ጠባር በር ሆነ፡፡

ምንጊዜም ሀገራዊ መፍትሔ ውጤታማ የሚሆነው ሀገር ከመፍረሷ በፊት ከተከናወነ ነው፡፡ በኢራቅ፣ በአፍጋኒስታን፣ በሶማልያና በኮንጎ የምናየው ነገር ይኼንን ይነግረናል፡፡ ሀገር ከፈረሰች፣ ሰው ደም ከተቃባ፣ ሀገራዊ ተቋማትም የሚመጣውን ችግር ሊሸከሙት ከማይችሉበት ደረጃ ከደረሱ በኋላ መፍትሔው ከሁሉም ወገኖች እጅ ይወጣል፡፡ አንድ በሽተኛ ሊድን የሚችለው በተቻለው ፍጥነት በቶሎ ወደ ሕክምናው ቦታ ከደረሰ ነው፡፡ በዘገየ ቁጥር የመዳን ዕድሉ እየጠበበ ይሄዳል፡፡ ሀገራዊ ችግርም እንደዚሁ ነው፡፡

አውስትራልያውያን ‹መድኃኒቱ የትኛችንም ፋርማሲ ውስጥ የለም› የሚሉት ነገር አለ፡፡ ሰሞኑን በሀገራቸው የምርጫ ዘመቻው ተጀምሯል፡፡ ዋናው አጀንዳቸው የሆነውን የሕገ ወጥ ስደት ጉዳይ ሲከራከሩበት ነበር ይህን ያሉት፡፡ በሀገሪቱ ያሉት ፓርቲዎች ሥልጣን በያዙ ቁጥር ሕገ ወጥ ስደትን ያስቆማል የሚሉትን መፍትሔ ሁሉ ወስደዋል፡፡ በየወሩ 1440 ስደተኞች በጀልባ ለሚገቡባት አውስትራልያ ግን የማንም ፓርቲ መድኃኒት ፍቱን መድኃኒት ለመሆን አልቻለም፡፡ ‹‹ችግሩን ለመፍታት የወሰድናቸው መንገዶችም አልፈቱትም፡፡ ሁሉንም መድኃኒት ሞክረናል፤ ግን በሽታው አልዳነም፡፡ ስለዚህ ሌላ መድኃኒት ነው የሚያስፈልገን፡፡ መድኃኒቱ ደግሞ በየትኛውም ፋርማሲ ውስጥ የለም›› ነው ነገሩ፡፡ አዲስን በሽታ በድሮ መድኃኒት ማከም በሽታውን ራሱን ማወሳሰብ ነው፡፡ እናስ? ከተባለ የተለመደውን የመድኃኒት ማዘዣ እየጻፉ የማያድን መድኃኒት ከመስጠት ይልቅ፣ አዲስ መድኃኒት እንፈልግ፣ እንፈልስፍ፡፡ ለዚህ ደግሞ የሁሉም የመድኃኒት ዐዋቂዎችን ዕውቀትም፣ ትጋትም፣ ዐቅምም፣ ቆራጥነትም ይፈለጋል፡፡

ነባር መድኃኒት የሚሠራው በሽታው መድኃኒቱን ሳይለምደው ወይም በሽታ ከዐቅም በላይ ከመሆኑ በፊት ነው፡፡ ያን ጊዜ ከሆነ ከአንዱ ፋርማሲ የተሻለውን መድኃኒት ገዝቶ መውሰድ ይቻላል፡፡ በሀገራችን እንደሚደረገው የሕንድ ነው፣ የቻይና ነው፣ የጀርመን ነው፣ የእንግሊዝ ነው፣ የአሜሪካ ነው፣ የደቡብ አፍሪካ ነው? ብለን የተሻለውን መድኃኒት ገዝተን እንውጣለን፡፡ በሽታው ከዐቅም በላይ ሲሆን ግን ሌላ አዲስ መድኃኒት ነው የሚጠይቀው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በሽታው ራሱ አዲስ ስለሚሆን፡፡ ያለበለዚያ አዲሱን ወይን ጠጅ በአሮጌ አቁማዳ ይሆናል፡፡

ሞያ ከጎረቤት ነውና ሀገራችን ከጎረቤት ግብጽ መማር ያለባት ይመስለኛል፡፡ አሁን መድኃኒቱ ከሁሉም ወገኖች ፋርማሲዎች ውስጥ ያለ አይመስልም፡፡ ሀገራዊ ችግሮቻችንን ለማከም በድሮ መድኃኒቶች ነው እየተጠቀምን ያለነው፡፡ አንዳንድ መድኃኒቶች በንጉሡ ጊዜ፣ በወታደራዊው መንግሥት ጊዜ፣ በነጭ ሽብርና ቀይ ሽብር ጊዜ፣ በአሲምባና በደደቢት፣ ተሞክረው ያልሠሩ ናቸው፡፡ በኢዲዩ፣ በኢሕአፓ፣ በመኢሶን፣ በኢጭአት፣ በወዝ ሊግ፣ በአኢሴማ፣ በአኢወማ፣ በ66ና በ97 ተሞክረው ማዳን ያቃታቸው ናቸው፡፡ በሽታው ግን አዲስ ነው፡፡

አሁን የሚበጀን የእኔ ፋርማሲ ውስጥ ያለው መድኃኒት ፍቱን ነው ማለቱን ትቶ ለአዲሱ በሽታ አዲስ መድኃኒት ለመፍጠር መነሣት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሁሉንም ዕውቀት፣ ትጋት፣ ቁርጠኛነትና ዐቅም ይጠይቃል፡፡ ሀገር የአንዱ ወገን ብቻ ልትሆን አትችልም፡፡ ሀገር የሁሉም ካልሆነች የማንም አትሆንም፡፡ ያለበለዚያ ግን በግብጻውያን ላይ እንደምናየው ሁላችንም ወደ ጽንፍ ሄደን ‹እንትን ወይም ሞት› ካልን ሁላችንም ሥጋውን እናጣውና ያልታሰበ ቡችላ ነጥቆ የሚሄድበትን ዕድል እናመቻቻለን፡፡ መድኃኒቱ የሁላችንም ፋርማሲ ውስጥ ያለ አይመስልም፡፡ የሚበጀው የእኔን መድኃኒት ብቻ ካልዋጥክ አትድንም የሚለው አሮጌው መፍትሔ ሳይሆን መድኃኒቱን ሊያስገኙ የሚችሉትን አካላት ሁሉ ተጠቅሞ ለአዲሱ በሽታ አዲስ መድኃኒት መፈለግ ነው፡፡   

የሀገርን ክብር ከፍ የሚያደርጉ፣ ጽናትንና ብርታትን የሚሰብኩ፣ አልበገር ባይነትንና ተጋድሎን የሚያውጁ፣ ለዓላማ ቁርጠኝነትንና ትጋትን የሚናኙ የተባረኩ እግሮች፡፡ ምን ነበር ይሆን የምታስቢው እንዲያ ተከበሽ ስትሮጭ፣ ምን ነበር ይሆን የምታልሚው እንዲያ ሀገርሽ አንድ ወርቅ እንኳን አጥታ ስሟ ከሠንጠረዡ ሲጠፋ፤ ምን ነበር ይሆን የምታስቢው የእነ አበበና የነ ማሞ፣ የነ ምሩጽና የነኃሌሌ፣ የነ ቀነኒሳና የነ ገዛኸኝ ታሪክ ወደ ተረትነት ሲለወጥ፤ ተንታኙ ሁሉ እንዲህ ነበሩኮ የሚለንን ስትሰሚ ምን ነበር ይሆን የምታስቢው፡፡

የሮጥሽውን እንጂ ያሰብሽውን አላየነውም፡፡ ያደረግሽውን እንጂ የወሰንሽውን አልተመለከትነውም፡፡ ወደየት ነበር የሮጥሽው? ምን ነበር ከፊት የሚታይሽ? አበበ ነው ወይስ ኃይሌ? ባንዲራሽ ነው ወይስ ሕዝብሽ? መቼም ምንመ ሳታይ እንዲያ አልተፈተለክሽም፡፡ ምንስ ነበር የምትሰሚው? መቼም የሞስኮን ሕዝብ ጩኸት አይደለም፡፡ በማያውቁት ቋንቋ የሚነገር ጩኸት ምች እንዲያ ያስሮጣልና፡፡ ሂጂ፣ ሂጂ፣ ሂጂ ጥሩነሽ ሩጭ፤ ታሪክ ተረት ሆኖ እንዳይቀር ለሀገርሽ ወርቁን አምጭ› ‹ሂጅ አብረንኅ እየሮጥን ነው፣ ብቻሽን ከቶ አይደለሽም፤ ምሩጽ ቀድሞ ሰባብሮታል፣ ይህ አየር ለኛ አዲስ አይደለም› የሚለው የሕዝብሽ ድምጽ ነበር በሹክሹክታ የተማሽው? አርምሞኮ ቋንቋ ነው በውስጥ ከነፍስ ጋር የሚያወሩት፡፡

እነዚያ እግሮችሽ እንደ ሲላ ሲወረወሩ፣ እንደ ንሥር ሲበርሩ፣ እንደ አቦ ሸማኔ ሲፈተለኩ፣ እንደ ሚግ ሲምዘገዘጉ፣ እጆችሽ እንደ መልአክ ክንፍ አየሩን ሲሰነጥቁ፣ ደረትሽ እንደ ሚሳይል እየከፈለው ሲተኮስ፤ እንደታቀፈች ሰጎን ዓይኖችሽ ምድር ምድር ሲያዩ፣ ከአየር ጋር ስትሟገች፣ ከድል ጋር ስትጠራሪ፣ ከእልክ ጋር ተወራርደሽ፣ ከእምቢ ጋር አብረሽ ስትሮጭ፤ ልብና እግሮችሽ ተስማምተው እየተማከሩ ሲነጉዱ፤ ዓይንና እጆችሽ ተፋቅረው የርቀት መጠን ሲለኩ፤ እንደ ንብ አውራ ታጅበሽ፣ እንደ ንብ ንግሥት ስትከንፊ፤ ምነ ነበር ያኔ የምታስቢው?

ሀገር ነበረች ከኋላሽ፣ ሀገር ነበረች ከፊትሽ፤ እንዳንች ማልያ አጥልቀን፣ እንዳንቺ ሞስኮ ባንጓዝ፤ እንዳንቺ ሀገር ወክለን እንዳንቺ በመም ላይ ባንከፍ፤ ልባችን ካንች ጋር ነበር፣ ሁሉንም ዙር አብሮ ዞሯል፤ ኅሊናችንም ካንቺ ጋር ለአምላክ ሥዕለቱን አቅርቧል፡፡ እንዴት ደስ ይላል መሰለሽ አገር አስከትሎ መሮጥ፤ እያባረርሽን አልነበረም፣ እየተከተልንሽ እንጂ፣ በእጅሽ መሣሪያ አልያዝሽም፤ ውርደትን ቀዘፍሽው እንጂ፡፡ ሀገርን ሊያኮራ የሚሮጥ፣ ድሮም ሕዝብ አብሮት ይሮጣል፣ እግሮቹ ብሩካን ናቸው ብሎ ከጥንቱ መርቆታል፡፡ በሞስኮ አፈር ላይ አይደለም በብሩካን እግሮችሽ የሮጥሽው፣ በሚወድሽና በሚሳሳልሽ ሕዝብ በልቡናቸው ውስጥ ነው፡፡


አብረንሽ ባንሮጥ ኑሮ ድል ስታደርጊ ለምን አብሮ ደስ አለን? ድል አደረግን ሲሉንኮ አብረናቸው ያልተደሰትን ብዙዎች አሉ፡፡ ድሉ የራሳቸው ብቻ የሆነ፤ ብቻቸውን ያሸነፉ፤ ድላቸውን ያልገዛንላቸው፡፡ አንዳንዶች ወርቅ ከሀገራቸው ሲያወጡ አንቺ ግን ወርቅ ወደ ሀገርሽ አመጣሽ፤ ስለዚህ አብረንሽ ሮጥን፡፡ አብረንሽም ስለሮጥን አብረንሽ ተደሰትን፡፡ ሞስኮ ላይ ያዩሽ ሁሉ፤ ምሩጽ አልሞተም አሉ፡፡ አረንጓዴው ጎርፍ ቢደርቅም አረንጓዴ ወርቅ አላቸው አሉ፡፡ ሁሉንም የሚግባባ ሃሳብና ፕሮግራም፣ አስተዳደርና አመራር፣ አካሄድና መዋቅር በጠፋበት ጊዜ ምሥራቅ ከምዕራብ ሰሜን ከደቡብ አስተባብረሻልና የመግባቢያ ሰነዳችን ሆነሻል፡፡ በየጎራው የቆሙትን፣ በየተቃራኒው የተሰለፉትን ሁሉንም ሞስኮ አምጥተሸ አንድ አድርገሻቸዋልና የአንድነት ዓርማ ሆነሻል፡፡ 

ማጭበርበር በሌለው ምርጫ ተመርጠሻል፤ የምረጡኝ ዘመቻ ሳያስፈልግሽ በተግባር ሕዝብ አሰልፈሻል፤ ዙፋን ሳያስፈልገሽ ነግሠሽ፣ ሉል ሳያስፈልግሽ ገዝተሻል፡፡ ስም ወደ ግብር ይመራልና ጥሩነሽ ጀግና ሆነሻል፡፡

እግሮችሽን አበርትቶ፣ ጣቶችሽን ያለምልማቸው፣ ኅሊናሽን አንቅቶ፣ ለዓይኖችሽ ብርሃን ይጨምርላቸው፤ የልብሽን ምት ጠብቆ እጆችሽን አክናፍ ያርጋቸው፤ ሳትደክሚ ምትክሽን፣ ሳታርፊ ደቀ መዝሙርሽን ያሳይሽ፡፡ ቀና እንዳደረግሽን ቀና በይ፣ እንዳከብርሽን ይክብርሽ፤ እንዳኮራሽን ያኩራሽ፤ እንዳደመቅሽን ያድምቅሽ፡፡ 

አውሮፕላኑ ወደ ምድር ዝቅ እያለ መሆኑን አስተናጋጇ በመናገር ላይ ናት፡፡ የምናርፈው ባንዳር ሰሪ ባጋዋን የሚባለው የብሩናይ ዓለም ዐቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ነው፡፡ ብሩናይ እስከ ዛሬ ስሟን እንኳን ሰምቻት የማላውቅ ትንሽ የደቡብ እስያ (ኦሺንያ) ሀገር ናት፡፡ ወደ እርሷ ለመድረስ ከዱባይ ተነሥተን የ8 …

ጉዞ ወደ ምድር ጥግ (ሦስተኛ ክፍል) Read more »

ነፍሱን ይማረውና ሀገራችን ካፈራቻቸው የቅርብ ዘመን ገጣምያን አንዱ ደበበ ሰይፉ ‹ከአኩስም ጫፍ አቁማዳ›› የሚል ግጥም ነበረው ፡፡በዚህ የኢትዮጵያዊነት ፍቅርና መነሻውን በውብ ትረካ በገለጠበት ግጥሙ ላይ እንዲህ የሚሉ የመዝጊያ አካባቢ ስንኞች አሉት፡፡ ‹‹እኔ ና ወንድሞቼ›› አለ በለዘብታ ለራሱ እንዲያወራ የራሱን ስሞታ …

ባዶ አቁማዳ Read more »

ከምሽቱ አራት ሰዓት ተኩል ላይ ወደ አውሮፕላኑ እንድንገባ ተጋበዝን፡፡ በቀኜም በግራዬም ከፊቴም ከኋላዬም የተቀመጡት የእስያ ዝርያ ያላቸው ተጓዦች ናቸው፡፡ እንዲህ ኤስያውያን በሞሉበት አውሮፕላን ስሄድ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ አስተናጋጆቹ ከዚህ በኋላ ወደ ቀጣዩ መዳረሻችን ለመድረስ የስምንት ሰዓት ከሩብ ጎዳና ይቀረናል አሉ፡፡ ከዚያ በኋላ ደግሞ ሌላ አውሮፕላን እንይዛለን፡፡ ድሮ ሦስተኛ ክፍል ስንማር ‹ንብ አበባ ለመቅሰም የምታደርገውን ጉዞ በአንድ መሥመር ብታደርገው ኖሮ፣ ዓለምን ትዞር ነበር› የሚል ነገር ተምሬ ነበር፡፡ አሁንም የኔ ነገር እንደዚያ ሳይሆን አይቀርም፡፡

‹ይህ ነው ምኞቴ እኔ ለሕይወቴ› የሚል የቆየ የማርሽ መዝሙር  ትዝ አለኝ፡፡ እዚያ መዝሙር ውስጥ ደግሞ

ረዥሙን ጉዞ ትግሉን ዐውቄ

ተነሥቻለሁ ትጥቄን አጥብቄ

የሚል ነገር ነበረው፡፡ ምን ይደረግ ሰው ከሀገሩ ሲወጣ ትዝታ ነው የሚተርፈው፡፡ ከወሎ መቄት ወደ አዲስ አበባ መጥተው የኖሩት አለቃ ለማ ኃይሉ አይደሉ እንዴ ቢቸግራቸው ‹‹እግር አዲስ አበባ ልቡና መቄት›› ያሉት፡፡ አንዳንድ ጊዜ ‹ሀገር ማለት ምንድን ናት?›› ያሰኛል፡፡ በሀገራችን ተሰቃየን፣ ታሠርን፣ ተንገላታን፣ ግፍ ተፈጸመብን ብለው ከሀገር የሚወጡ ወገኖቻችን እንኳን መልሰው ‹ሀገሬ› ሲሉ ሳያቸው ይህቺ ሀገር የምትባል ‹መንፈስ› ምንድን ናት? እላለሁ፡፡ አንድ ጊዜ ከዋሽንግተን ዲሲ ወደ አዲስ አበባ ስመጣ ከጎኔ አንድ በጎልማሳነት እድሜ ላይ የደረሰ ኢትዮጵያዊ ወገን ተቀምጦ ነበር፡፡ አውሮፕላኑ ሲነሣ እጁ ይንቀጠቀጣል፡፡ ያመመው መሰለኝና ዘወር ብዬ ‹‹አመመህ›› ስል ጠየቅኩት፡፡ ግንባሩን በመሐረብ እየጠረገ ‹‹ደኅና ነኝ፣ ምንም አልል›› አለኝ በእንግልጣር፡፡ አሁንም እጁ ይንቀጠቀጣልና ዘወር አልኩ፡፡

‹‹ይገርምሃል ከሀገሬ ከወጣሁ ሠላሳ ዓመቴ ነው፡፡ ወደ ሀገር ለመሄድ ሳስብ ሁልጊዜ ሰውነቴ ይንቀጠቀጣል፡፡ አንዳች ነገር መጥቶ ይወርረኛል፡፡ ልቤ ምቱ ይጨምራል፡፡ አሁንማ አውሮፕላን ውስጥ ስገባ ባሰብኝ፡፡ ውስጤ ብርድ ብርድ ይለኛል፤ እንደገና ይሞቀኛል፡፡ ምን እንደሆነ ማወቅ አልቻልኩም›› አለኝ፡፡ እያየሁት እገረም ነበር፡፡ ከሕይወቱ አብዛኛውን፤ ያውም ነፍስ ያወቀበትን ዘመን ያሳለፈው አሜሪካ ነው፡፡ ግን ‹ኢትዮጵያ› የሚለውን ሲያስበው አንዳች ስሜት፣ እርሱም የማይገባው ስሜት ይወርረዋል፡፡ ‹‹ሀገር ምንድን ነው?››

ደግነቱ አንድ ወዳጄ ‹‹ዜጋን ከሀገሩ ማስውጣት ቀላል ነው፤ ሀገርን ከዜጋው ልብ ማስውጣት ግን አይቻልም›› ብሎኝ ነበር፡፡ እኛ ልብ ውስጥ ልዩ የሆነች ሀገር አለች፡፡ ማንም የማይነካት፣ ማንም የማይወስዳት፣ ማንም የማያጠፋት፡፡ አለቃ ለማ ‹ልቡና መቄት› ያሉትኮ መቄት ከልባቸው አልወጣ ብላቸው ነው፡፡

ይህንን ሁሉ እያሰብኩ አውሮፕላኑ ተነሥቶ ወደ ሕንድ ውቅያኖስ አቅጣጫ ማምራት ጀመረ፡፡ እኔም የሕይወት ተፈራን Tower In The Sky አውጥቼ ማንበብ ጀመርኩ፡፡ ያ ትውልድ አሁንም አብሮኝ ሕንድ ውቅያኖስን ሰንጥቆ ሊጓዝ ነው፡፡ ዓላማ፣ ትጋት፣ ቆራጥነት፣ መሥዋዕትነት፣ ጽንዓት የነበረው አንድ ትውልድ ጠፍቷል፡፡

በማርክሲስት ሌኒኒስት ቀንበር ተቀይዶ፣ የሁሉንም ነገር መፍትሔ ከመጻሕፍት ውስጥ ሲያስስ፣ እርስ በርስ ተከራክሮና ተወያይቶ በመተማመን ወይም ባለመተማመን መፍታት ሲቻል፤ ተምሮ እንዳልተማረ፣ ዐውቆ እንዳላወቀ ሲጨራረስ ማየት አሳዛኝ ነው፡፡ ሁሉንም ነገር በሳጥን ውስጥ ብቻ ለመመልከት የሚተጋ ትውልድ የ‹ኢስት› ብዛት፡- ማርክሲስት፣ ማኦኢስት፣ ቾቭኒስት፣ ፌሚኒስት፣ ካፒታሊስት፣ አናርኪስት፣ ፋሺስት፣ ትሮትስኪስት፣ ኮሙኒስት፣›› የ‹ኢዝም› መዓት፡፡ ሁሉንም ሃሳቦች፣ ሁሉንም አመለካከቶች በሳጥኖች ብቻ አድርጎ የመመልከት አባዜ፡፡ ማርክስ፣ ሌኒንና ኤንግልስ የሚባሉ ሐዋርያት ያመጡት አዲስ ሃይማኖት፤ ቦልሼቪስት፣ ማኦኢስት፣ ማርክሲስት የሚባሉ ምእመናን፤ አናርኪስት፣ ትሮትስኪስት፣ የሚባሉ መናፍቃን፤ ኢምፔሪያሊስት፣ ፊውዳልና ቡርዧ የሚባሉ አጋንንት፣ ተፈጥረው አማኝና ከሃዲ ሲወጋገዙና ሲጫረሱ የኖሩባቸው ዘመናት፡፡

መጽሐፉ እያሳዘናችሁ እያስገረማችሁ፣ እያበሳጫችሁም ይጓዛል፡፡ የአንድ ፓርቲ ሰዎች ትናንትም ይከፋፈላሉ፤ ዛሬም እንዲሁ፤ ተከፋፍለውም ይወጋገዛሉ፤ ዛሬም እንዲሁ፤ ተወጋግዘውም ይገዳደላሉ፤ ዛሬም እንዲሁ፤ ለአብዮቱ ሲባል፤ ለትግሉ ሲባል፤ አድኅሮት ኃይላትን ለማስወገድ ሲባል በጓዶች ላይ ርምጃ ይወሰዳል፡፡ ድመት ይመስል አብዮት ልጆቿን ትበላለች፡፡ እስካን አይጥ ለማጥመጃ ስንት መሣሪያ ሲሠራ፤ ምነው ይህቺን ልጆቿን የምትፈጅ ‹የአብዮት ድመት› ማጥፊያ መድኃኒት ጠፋ?

የዚያ ዘመን ሰዎቹ ዐልፈዋል፤ ሥርዓቱ ዐልፏል፤ ታሪኩ ዐልፏል፤ መንፈሱ ግን አለ፡፡ ‹‹ግደል ተጋደል በርታ ወገኔ›› የሚለው ዛር ግን አለ፡፡ ፖለቲካዊ ጽንፈኛነት፤ ደጋፊነትና ጠላትነት፤ ሥር ነቀልነትና ደምሳሽነት አሁንም አሉ፡፡ ይህንን መንፈስ የሚያጠፋ ትምህርት፤ የሚደመስስ ጸሎት፤ የሚያስቀር ሥርየት አልተገኘም፡፡

መጽሐፉን እንዲህ እያነበብኩ እያለ አስተናጋጆቹ ምግብ ይዘው በጎናችን መጡ፡፡ ከጎኔ ላለው ሰውዬ የሰጠችው ምግብ ስሙን የጠራችው በቻይንኛ ሳይሆን አይቀርም፡፡ የነዚህ የእስያውያን ነገርኮ ምን እንደሚበሉና ምን እንደማይበሉ አይታወቅም፡፡ ቢጨንቀኝ ዓሣ አዘዝኩ፡፡ የመጣውን ነገር አልነግራችሁም፡፡ ምናልባት ምግብ ላይ ትሆናላችሁና ይቅር፡፡ አንድ ወዳጄ ‹‹እነዚህ ሰዎችኮ ሰውን ባሕር ውስጥ ቢያገኙት ዓሣ ነው የሚሉት›› ያለኝ ትዝ አለኝ፡፡ እንኳን ልበላው ኢትዮጵያ የበላሁትም ምግብ ሆዴ ውስጥ ሆኖ እንደ ኤርታሌ ይተራመስ ጀመር፡፡

ከድኜ ተውኩትና መጽሐፉን ቀጠልኩ፡፡ አይ ሕይወት እግዜር ይይልሽ፡፡ ልደታ ብስኩት ቤት፣ ፒያሳ ጮርናቄ ቤት፣ ሐረር ምግብ ቤት፣ ምናምን ክትፎ ቤት እያለች የአዲስ አበባን ምግብ ቤቶችና ሻሂ ቤቶች ትዘረዝራለች፡፡ ይህም አልበቃ ብሏት በመቀሌ መንገድ ላይ ‹‹ምን የመሰለ ዱለት በላሁ›› ትላለች፡፡ እኔ እዚህ በአንድ በኩል የሚዘጋ ምግብ ከፊቴ ተቀምጦ ይተናነቀኛል፤ በሌላ በኩል ደግሞ የሀገሬን ምግብ ቤትና ምግብ እያነበብኩ ረሃቤ ይቀሰቀስብኛል፡፡ ተርቦ ስለ ረሃብ ማንበብን የመሰለ ቅጣት መቼም የለም፡፡

ዘሚካኤል ትዝ አለኝ፡፡ ዘሚካኤል ኤርትራዊ ነው፡፡ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ከዐሥራ ሁለት ዓመታት በፊት ባዘጋጀው አንድ ሴሚናር ላይ ለመሳተፍ ተጋብዘን ኡጋንዳ ኢንሴንዜ የምትባል መንደር ተገናኝተን ነበር፡፡ እዚያ ከአሥራ ስድስት የአፍሪካ ሀገሮች የመጡ ወጣቶች ነበሩ፡፡ ከሁሉም የእኔና የዘሚካኤል የምግብ ምርጫ ነበር የሚገርማቸው፡፡ ከምንበላው የማንበላው ይበልጣል፡፡ አንደ ቀን ሴሚናር ላይ ውለን አምሽተን ተመለስን፡፡ እኔ ቀደም ብዬ ጨለም ወዳለው የማምሻችን ቦታ መጣሁ፡፡ እሳት ነድዶ ጨዋታው ቀልጧል፡፡ ዘሚካኤል መታጠቢያ ቤት ገብቶ ዘገየ፡፡ ስደርስ የሆነ ነገር ሸተተኝ፡፡ አሻግሬ ሳይ ጠረጲዛው ላይ ያለውን ነገር ይሻሙበታል፡፡ በጨለማው ውስጥ ያለው የእሳት ብርሃን ብቻ ስለነበር ልለየው አልቻልኩም፡፡ ራቅ ብዬ ተቀመጥኩ፡፡

ዘሚካኤል መጣና ጠረጲዛ ላይ ያለውን ነገር አየው፡፤ ‹‹ዘቢብ ሳይሆን አይቀርም›› አለኝ፡፡

‹‹አይ እኔ ይቅርብኝ አንተ ሞክረው›› አልኩት፡፡

‹‹ዘቢብ መሆን አለበት፤ መልኩ እንደዚያ ነው›› አለና ሊያመጣ ሄደ፡፡ ልክ ጠረጲዛው ጋ ሲደርስ ‹‹ቧ፣ አተ›› አለና ፈጠን ፈጠን ብሎ ወደ ማደሪያው ገባ፡፡ ምን ሆነ ብዬ ደነገጥኩና ተከተልኩት፡፡ ባንኳኳ ባንኳኳ አልከፍትም አለ፤ በስንት መከራ ሳስከፍተው ፊቱ በውኃ ርሷል፡፡

‹‹ምን ሆነህ ነው?›› አልኩት

‹‹ጉድ ሠሩኝኮ›› አለኝ

‹‹ምን አደረጉህ››

‹‹ምን እንደሆነ ዐውቀሃል››

‹‹ምንድን ነው?››

‹‹የተጠበሰ ክረምት አግባ›› በሳቅ ፈረስኩ፡፡ ለካስ እንደ ዘቢብ አምሮ የታየው እኛ ክረምት አግባ የምንለውን ሰብስበው ቆልተውት ነው››

ዛሬ የደረሰብኝ በዘሚካኤል በሳቅኩት ግፍ ነው፡፡

ከዱባይ ወደ ብሩናይ መንገድ፣ ሕንድ ውቅያኖስ ላይ


በከበደ ሚካኤልኛ እንዲህ ይተረካል፡፡
አንዲት ግልገል በቅሎ እናቷን እንዲህ ብላ ጠየቀቻት፡፡ ‹‹እማዬ እኔ ግን ማነኝ››
እናቷም ገረማትና ‹አንቺማ በቅሎ ነሽ፤ ግን ለምን ጠየቅሽኝ››
ግልገሏም ጥቂት ጊዜ ዝም ብላ ከቆየች በኋላ ‹‹መጀመሪያ ግን አህያ ነበርኩ ወይስ ፈረስ›› አለቻት፡፡ እናቲቱም አንገቷን ነቅንቃ፡፡ ‹‹እንስሳ ነሽ ልጄ፤ እንስሳ፡፡ ፈረስም አህያም እንስሳ ነው፡፡ ስንፈጠር እንስሳ ነበርን፡፡ የቤት የዱር፣ የሸክም የግልቢያ፣ የእርሻ የሜዳ፣ የንጉሥ የባሪያ የሚለው በኋላ የመጣ ነው፡፡ አዳምኮ ሲፈጠር ቤት አልነበረውም፡፡ ስለዚህ የቤት እንስሳ አልነበረም ማለት ነው፡፡ ሁላችንም ይህቺን ምድር እንደልባችን እንጠቀምባት ነበር፡፡ ነገር የመጣው በኋላ ነው፡፡ ለመኖር የሚደረግ ትግል ነው ይህንን አሁን ያለንበትን ሁኔታ የፈጠረው፡፡››
‹‹ጓደኛዬ የአንቺ አያቶች ጨቁነውናል አለኝ፡፡››

 ‹‹እንዴት አድርገው ነው የጨቆኑት፤ ለመሆኑስ የአንቺ አያቶች ስንት ናቸው? እርሱ የተነገረውን ብቻ ነው የሚያውቀው፤ ያልተነገረውስ? ከታሪካችንኮ በጣም ጥቂቱ ነው የተጻፈው፤ ከተጻፈውም በጣም ጥቂቱ ነው የተነገረው፡፡ ባልተጻፈው ታሪካችን ውስጥ ማን ምን እንደነበረ ማን ያውቃል? ለምሳሌ በሀገረ እሥራኤል አህዮች እጅግ የሚወደዱ የቤት እንስሳት ነበሩ፡፡ ነገሥታቱም፣ ካህናቱም፣ ነቢያቱም ዘመኑ ዘመነ ሰላም ሲሆን በአህያ ነው ይሄዱ የነበሩት፡፡ ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም የገባው በአህያ ነው፡፡ ድንግል ማርያም ወደ ግብጽ የተሰደደችው በአህያ ነው፡፡ በጥንታውያን ግብጾች ዘንድ አህያ የመኳንንትና የነገሥታት ሀብት ማሳያ ነበር፡፡ የናርማር ወይም  ሖር – አሃ መቃብር እንደሆነ በሚታመነው ቦታ ላይ በተደረገ ቁፋሮ አህዮች ከነገሥታቱ ጋር በክብር ተቀብረው ተገኝተዋል፡፡ በዚያ ጊዜ አህዮች የቤተ መንግሥቱን ምግብ እየተመገቡ፣ በቤተ መንግሥቱም እየተሸለሙ ኖረዋል፡፡ በሌላው ዘመን ደግሞ ይህንን ፈረሶቹ ወስደውታል፡፡››

‹‹ወደ ኋላ ተመልሰሽ ሁሉን እንስሳት ብታያቸው ታሪካቸው እንደዚሁ ነው ልጄ፡፡ በዘርሽ አትጨቁኝም፤ በዘርሽም አትጨቆኝም፡፡ የጭቆና መሠረቱ ኃይልና ሥልጣን ነው፡፡ አቤልን የገደለውኮ ቃየል ነው፡፡ የአንድ ማኅፀን ልጆች ናቸውኮ፡፡ ቃየል አቤልን የገደለው ለጥቅም ሲል ነው፡፡ እስኪ የሰዎችን ታሪክ እይው አፍሪካውያንኮ በራሳቸው በአፍሪካውያን ይጨቆኑ ነበር፡፡ ሥልጣን ላይ ያለው ሰው መሰሎቹን ይሰበስብና ሌሎቹን የሀገሩን ልጆች ይጨቁናል፡፡ መጀመሪያ የገዛ ወገኖቻቸውን ለዐረቦች በባርነት ሲሸጡ የነበሩት የሀገራቸው ሰዎች ነበሩ፡፡ አፍሪካውያን በባርነት ተሽጠው አሜሪካ ሲሄዱ ደግሞ ነጮቹ ጥቁሮቹን መጨቆን ጀመሩ፡፡ አየርላንዳውያን በእንግሊዞች መከራቸውን አይተዋል፡፡ ዓረቦች በዓረቦች ተሰቃይተዋል፡፡
አየሽ ቤተ መንግሥቱ ላይ ስትቀመጭ ሌላውን ለማግለል ሳጥን ትከፍቻለሽ፤ ከዚያ ሁሉንም በየሳጥኑ ታስቀምጭዋለሽ፡፡ የእምነት፣ የዘር፣ የመልክ፣ የአካባቢ፣ የቋንቋ ሳጥኖችን ከፍተው ሁሉንም እዚያ ስላስቀመጧቸው ተቀማጮቹ ሳጥኑን እንዳለ ተቀበሉት፡፡ ማንነታቸውም አደረጉትና ሳጥኑን ለማስቀረት ከመታገል ይልቅ ራሳቸውን ብቻ ከሳጥኑ ለማውጣት ይታገሉ ነበር፡፡ በሳጥኑ ዛሬ አህዮች ይገቡበታል፤ ነገ ፈረሶች፣ ከነገወዲያ ግመሎች፣ ከዚያም በጎች፣ ከዚያም ፍየሎች እየገቡበት ይቀጥላል፡፡ እኛም ዛሬ ያለሳጥን መኖር ከማንችልበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ እኔን ሲያገኙኝ እንስሳ መሆኔን አይደለም የሚያዩት፤ የትኛው እንስሳ? ይላሉ፡፡ – ፈረስ፡፡ በዚህ አያቆሙም፡፡ ከዚያ ደግሞ የትኛው ፈረስ? የዱር ወይስ የቤት? ይቀጥላል፡፡ -የቤት፡፡ ለጭነት ወይስ ለግልቢያ? መቋጫ የለውም ልጄ፡፡ በትልቁ ሳጥን ውስጥ ራሳችን የሠራናቸው ትንንሽ ሳጥኖችም አሉ፡፡ በእነዚያም ውስጥ ሌሎች ትንንሽ ሳጥኖች አሉ፡፡››
‹‹ ለአንድ የገጠር ጉዞ በእኔ ላይ ይሄድ የነበረ አንድ ሰው ሲናገረው የሰማሁትን ታሪክ ልንገርሽ፡፡ ሰውዬው የከባድ መኪና ሾፌር ነበረ፡፡ ድሮ አሰብ እየተመላለሰ ዕቃ ይጭን ነበር፡፤ አንድ ጊዜ ወደ አሰብ ሲሄድ በረሃው ላይ መኪናው ይበላሽበታል፡፡ ከዚያም እዚያው ማደር ስለነበረበት ለምግቡ የሚሆን ፍየል ከአካባቢው የአፋር ሰው ይገዛል፡፡ አፋሩ ሰውዬው ፍየሏን መሸጥ ብቻ ሳይሆን አርዶ፣ ጠብሶ ያቀርብለታል፡፡ ሾፌሩ ምግቡን እየበላ የሸጠለትን የአፋር ሰው ‹‹እንግዲህ ትቼህ መብላቴ ነው፤ እንብላ እንዳልልህ የክርስቲያን ሥጋ አትበላም ብዬ ነው›› ይለዋል፡፡ አፋሩ ሰውዬ ይገርመውና ‹‹እኔው አዋልጄ፣ እኔው አሳድጌ፣ እኔው አርጄ፣ እኔው ጠብሼ ያመጣኋትን ፍየል ምንጊዜ ክርስቲያን አደረግካት?›› አለኝ ብሎ ሲያወራ ሰማሁት፡፡ አየሽ ሌላን ማግለል ስትፈልጊ የሆነ ነገር ትፈጥሪያለሽ፡፡ ማቅረብም ስትፈልጊ እንደዚያው፡፡››
‹ብዙ ዓይነት ነጻ አውጭዎች አሉ፡፡ እኔ አሁን የፈረስ ነጻ አውጭ ውስጥ ልግባ ወይስ የአህያ? ወይስ የበቅሎ?›› አለቻት ግልገሏ፡፡
‹‹የእንስሳት ነጻ አውጭ ካለ እዚያ ግቢ፡፡ አንቺ እንስሳ ነሽ፡፡ የቀረው ከመኖር የመጣ ስም ነው፡፡ እንስሳት ሁሉ ነጻ ሳይሆኑ በቅሎ ተለይታ ነጻ ልትሆን አትችልም፡፡ አንድን አካቢ ብቻውን ንጹሕ ማድረግ አትችይም፡፡ ምክንቱም ዝንቧ ከወዲያኛው ማዶ ትመጣለችና፡፡ ከእኛም ወገኖችኮ ሜዳ በመኖራቸው የተነሣ ‹የሜዳ ፈረስ›› ተብለው የቀሩ አሉ፡፡ እኛ ከሰው ተጠግተን ‹የቤት ፈረስ›› ለመሆን ቻልን፡፡ ‹‹የቤት አህዮች›› አሉ፡፡ ‹‹የሜዳ አህዮች›.ም አሉ፡፡ የስም ጉዳይ ነው፡፡ የአኗኗር ጉዳይ ነው፡፡ በቤተ መንግሥት ከነገሥታት ጋር የሚኖር አንበሳ ነበርኮ፡፡ የነገሥታቱ ዙፋን እንዲያውም የአንበሳ ቅርጽ ነበረው፡፡ በዚያው ዘመን ግን ንጉሡ ጫካ ወጥተው ሌላ አንበሳ ገድለው እየተዘፈነላቸው ይመጣሉ፡፡ ጀርባሽን ለመጋለብ ምቹ ካደረግሽው ምንጊዜም የተሻለ ተወዳጅ ትሆኛለሽ፡፡ እንግሊዞች ‹‹Better to ride on ass that carries me, than on a horse that throws me – የምትገለብጠኝን ፈረስ ከምጋልብ፣ የምትሸከመኝን አህያ ብጋልብ ይመረጣል›› ይላሉ፡፡
ቤት የቀረው ውሻ ዱር ከቀረው ውሻ ጋር በመለያየታቸው ዛሬ አንዱ አንዱን እንደ ጠላት ያባርረዋል፡፡ ሰው ብልጥ ነው፡፡ አንዱን ወደራሱ አቅርቦ ውሻ አደረገውና ‹‹ቦቢ›› እያለ በማቆላመጥ ነጻ የወጣ አስመሰለው፡፤ ሌላውን ደግሞ ቀበሮ፣ ተኩላ ብሎ ጫካ ተወውና እርሱን መግደል ጀግንነት እንዲሆን አደረገው፡፡ አሁን ውሾቹ የሠለጠኑና ነጻ የወጡ መስሏቸው ተኩላና ቀበሮ ሲያብርሩ ይኖራሉ፡፡ አየሽ ጉዳዩ የዘር አይደለም፡፡ በዘር ከሰው ተኩላ ለውሻ ይቀርበዋል፣ ቀበሮ ይዛመደዋል፡፡ ጉዳዩ የጥቅም ጉዳይ ነው፤ የመደብ ጉዳይ ነው፡፡ ከቀበሮውና ከተኩላው መካከል ደግሞ የተወሰነውን ይወስዱና ፓርክ ውስጥ አስገብተው ያለፈለት ያስመስሉታል፡፡ እርሱም ማግኘት የሚገባውን ሳይሆን ራሱን ከጫካው ኑሮ ጋር ስለሚያነጻጽር ‹ተመስገን› እያለ ይኖራል፡፡››
‹‹ነጻነት የፍጡር ሀብት ነው፡፡ ለእነ እገሌ ተብሎ የሚቆረስ አይደለም፡፡ ጨቋኙም ተጨቋኙም ነጻ ካልወጣ ሙሉ ነጻነት አይገኝም፡፡ ጨቋኝነት ከአስተሳሰብ ባርነት የሚመጣ ነው፡፡ ከአመለካከት ድህነት የሚከሰት ነው፡፡ ሙሉ ነጻነትን ለማግኘት እርሱን ነጻ ማውጣት አለብሽ፡፡ ካልሆነ ግን ጉዞው አንዱን ጨቋኝ በሌላ ጨቋኝ መተካት ነው የሚሆነው፡፡ አፍሪካውያንኮ ራሳቸውን ከአውሮፓውያን ነጻ ማውጣት አላቃታቸውም፡፡ ያቃታቸው ራሳቸውን ከራሳቸው ነጻ ማውጣት ነው፡፡ ነጭ ጨቋኞች በጥቁር ጨቋኞች ተተኩ፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ ሳጥኑን ካላጠፋሽው ታግሎ ከሳጥኑ የወጣው ሁሉ በፋንታው የተሸነፈውን እርሱ ወደወጣበት  ሳጥን መክተቱ የማይቀር ነው፡፡
‹‹ደግሞስ ለምን በማትቀይሪው ነገር ጊዜሽን ታጠፊያለሽ? አሁን አንቺ በቅሎ ሆነሻል፡፡ አለቀ፡፡ ከእንግዲህ አህያ፣ ፈረስ፣ አንበሳ፣ ጅብ ፣ ድመት ልትሆኝ አትችይ? መሆን ለምትፈልጊው ነው መታገል ያለብሽ? በእጅሽ ላይ ላሉት ዕድሎች ነው መታገል ያለብሽ፤ ልትለውጫቸው ለምትችያቸው ዕድሎች ነው መታገል ያለብሽ፤ ልታሸንፊያቸው ከምትችያቸው ነገሮች ጋር ነው መታገል ያለብሽ፡፡ ትናንትን በነገ ለመቀየር ታገዪ፤ ትናንት ውስጥ ገብተሸ ግን እቀይረዋለሁ አትበዪ፤ መጀመሪያ አንቺ ራስሽ ከትናንቱ ውጭ፤ ያ ያለፈ ነገር ነው፡፡ ታሪክ አይታረምም፤ ሆኗልና፡፡ በታሪክ ውስጥ የተፈጠረ ችግር ግን በቀጣይ ታሪክ ይታረማል፡፡ ምን ሆነ? የሚለው አይለወጥም፤ ምን ይሁን? የሚለውን መለወጥ ግን ይቻላል፡፡ ዛሬ ላይ ሆነሽ የመጣሽበትን ማስተካከል አትችይም፤ የሚትሄጅበትን ግን ትችያለሽ፡፡ ብዙዎቹ ነጻ አውጭዎች ትናንትን ነጻ ለማውጣት የተቋቋሙ ናቸው፡፡ አንቺ መግባት ያለብሽ ነገን ነጻ ሊያወጣ የተቋቋመ አካል ከተፈጠረ ብቻ ነው፡፡
‹‹አፍሪካውያን ‹‹until the lions have their own historians tales of hunt will always glorify the hunters- አንበሶች የራሳቸው ታሪክ ጸሐፊዎች እስኪኖሯቸው ድረስ ስለ አደን የሚጻፈው ታሪክ ሁሉ ምጊዜም አዳኞችን የሚያገንና የሚያከብር ይሆናል›› ይላሉ፡፡ ዛሬ ከአንድ ወገን ብቻ እየሰማን የምንፈርዳቸው ፍርዶች በታሪክ ተሠሩ ከምንላቸው ስሕተቶች በላይ እንድንሳሳት የሚያደርጉን ናቸው፡፡ የማናውቃቸውና ያልሰማናቸው፤ ምናልባትም ወደፊትም ልንሰማቸው የማንችላቸው ታሪኮችም አሉን፡፡ ትናንት ያለፈ በመሆኑ ለፍርድ እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ሰሎሞን ዴሬሳ የተባለ ሰው ‹አንተ ዘርህ ምንድን ነው?› ሲባል ‹‹በቅድመ አያቴ ደጅ ማን እንዳለፈ እኔ ምን ዐውቃለሁ›› ይል ነበር፡፡ በአንቺስ ቅድመ አያት በር ማን እንዳለፈ ምን ታውቂያለሽ? መጠኑና ዘመኑ ይለያያል እንጂ ‹ሌላ› የሚለውን አካል ሳይገድል፣ ሳያጠፋ፣ ሳይጨቁን፣ ሳይቀማ እዚህ የደረሰ የለም፡፡ ግን ታሪክ እንደተራኪው ነው፡፡
‹‹ሁላችንንም መከራውና ግፉ፣ ጭቆናውና የደረሰብን ነገር ሁሉ አስተባብሮናል፡፡ በየዘመናቱ ቤተ መንግሥቱን የተጠጋ ተሸልሟል፡፡ አምሮበታል፡፡ ሌላውን ለማስገበርም ዘምቷል፡፡ እኛ አህዮች፣ ፈረሶችና በቅሎዎች ነንኮ ሌሎች እንስሳት እንዲታደኑ አብረን ከሰዎች ጋር የዘመትነው፡፡ በእኛ ዘምተው ሌላ ሀገር የሚገኙ ፈረሶችንና አህዮችን እንዲዘርፉ አድርገናልኮ፡፡ ከዘመቻው በኋላ ለእኛ የተሻለ ነገር ጣል ሲደረግልን እነርሱ ግን በባዶ ሜዳ አድረዋልኮ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ለእኛ እነርሱ ይቀርቡን ነበር፡፡ ነገር ግን ቤተ መንግሥቱን ስትጠጊ እንዲህ አታስቢም፡፡ በታሪካችን ውስጥ የደረሱብንንና ያደረስናቸውን ብንቆጥራቸው ከምንለያይበት የምንመሳሰልበት ይበልጣል፡፡ ግን ምን ያደርጋል ከሳጥኑ ወጥቶ የሚያስብ የለም፡፡ ሳጥኑ ውስጥ ስትሆኚ ደግሞ ያንቺ ብቻ ነው የሚታይሽ፡፡
‹‹መቼም በእንስሳት ታሪክ ቀደምት ከሚባሉት አንደኛዎቹ ቲቤታውያን ናቸው፡፡ እንዲህ ይላሉ ‹‹አንጥረኛው ጥበበኛ ከሆነ ብረትና ነሐስ ሊዋሐዱ ይችላሉ››፡፡ አሁንም እኛ አንድ ልንሆን ያልቻልነው አንድ የሚያደረግን ነገር ስለሌለ ሳይሆን አንድ የሚያደርገን ጥበበኛ አንጥረኛ ስለሌለ ነው፡፡ እስኪ ተመልከቺው፤ ቤተ መንግሥት የኖረውን አንበሳኮ ነው ‹‹አንበሳ ሲያረጅ የዝንብ መጨዋቻ ይሆናል›› የሚሉት፡፡ ታድያ ከጫካው አንበሳ ምን የተለየ ነገር አገኘ? የቤት አህያም ሆነ የጫካ አህያ ሲያረጁ ሁለቱንም አውሬ ይበላቸዋል፡፡ ቤት ውስጥ የኖረውም ውሻ ሲያረጅ ዞር ብሎ የሚየው የለም፡፡ ስለዚህ ልጄ አሁን የሚያስፈልገን የእገሌ ነጻ አውጭ ድርጅት ሳይሆን ‹የአስተሳሰብ ነጻ አውጭ ድርጅት›› ነው፡፡ አስተሳሰብሽ ነጻ ሲወጣ ‹‹መጀመሪያ እኔ እንስሳ ነኝ ወይስ በቅሎ?›› የሚለውን ጥያቄ ራስሽ ትመልሽዋለሽ፡፡
ሲድኒ፣ አውስትራልያ

ከአዲስ አበባ ወደ አውስትራልያ ልጓዝ ነው፡፡
ትነሣላችሁ የተባልነው ከምሽቱ አራት ሰዓት ከ15 ነበር፡፡ ‹ነበር› ካልኩ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ የመሳፈሪያው አዳራሽ ውስጥ ተቀምጠን ግን የመሳፈሪያው ሰዓት በረረ፡፡ ሰዓቱ እኛን ጥሎን በሌላ አውሮፕላን ይብረር፣ ወይም የመሳፈሪያውን ሰዓት ያደረገው የአየር መንገዱ ሠራተኛ ሳይመጣ ይቅር የታወቀ ነገር የለም፡፡ ደግነቱ የአየር መንገዱም ሠራተኞች የተሰጣቸው መመሪያ ‹‹የመሣፈሪያ ሰዓት ካለፈ ምንም ነገር እንዳልተፈጠረ ሳታስነቁ ወዲያ ወዲህ ማለት ነው› የሚል ሳይሆን አይቀርምና አንዳቸውም ምን አልተነፈሱም፡፡
መቼም ኢትዮጵያ ውስጥ መረጃ ለማግኘት የሚታወቅ መንገድ (system) ስለሌለ የሚታወቅ ሰው መፈለግ ነው፡፡ አንዱን የማውቀውን ሰው ጠጋ ብዬ ስጠይቀው ለንደን ላይ አውሮፕላናችን መጠነኛ ችግር እንደገጠመው ሹክ አለኝ፡፡ ምናልባት በዚያ ተደናግጠው ይሆናል ብዬ ይቅር አልኳቸውና መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ከጥቂት ጊዜ ቆይታ በኋላም ሕዝቡን ወደ ስታዮም እንደሚገባ ተመልካች አንጋግተው ይዘውት ወረዱ፡፡ ‹‹ሕጻናት ያላችሁ፣ የቢዝነስ ክፍል አባላት፣የሼባ ማይልስ የወርቅ አባላት›› ብሎ ነገር የለም፡፡ ‹‹እየየ ሲዳላ ነው›› አሉን፡፡ የሰው ጎርፍ ወደ ታችኛው ፎቅ በደረጃው ፈሰሰ፡፡ 

በአውቶቡሱ በኩል ተሸጋግረን ወደ አውሮፕላኑ ገባን፡፡ የመቀመጫ ለውጥ እንጂ የሰዓት ለውጥ አልነበረውም፡፡ ለነገሩ ብዙ ጊዜ በሀገሪቱ የመቀመጫ ለውጥ ነው የሚመጣውና አልተገረምንም፡፡ ‹መሣፈሪያ አዳራሹ ውስጥ መቀመጥ ሰለቸን› ያልናቸው ይመስል አውሮፕላኑ ውስጥ አንድ ሰዓት አስቀመጡን፡፡ ደግነቱ አብራሪው እየደጋገመ ይቅርታ ይጠይቃል፡፡ ከተለያየ ሀገር የሚመጡ ተሸጋጋሪ መንገደኞች እየተጠበቁ መሆኑንም ይነግረናል፡፡ መቼም የመጣውን አስቀምጦ ያልመጣውን መጠበቅ የተለመደ ነውና አላዘንኩበትም፡፡ ሠርግም ላይ፣ ስብሰባም ላይ፣ ጉባኤም ላይ፣ ግብዣም ላይ በሰዓቱ አክብረው የመጡት የዘገዩት እስኪመጡ እንዲጠብቁ በሚደረግበት ባህል ውስጥ ስላለን የሚገርም አይደለም፡፡
ከመቅረት መዘግየት ይሻላል ብሎ አውሮፕላኑ ወደ ዱባይ ተነሣ፡፡ ከጎኔ አንዲት እንደኔ አፍሪካዊት የሆነች፣ እንደ እኔ ግን ኢትዮጵያዊት ያልሆነች ሴት ተቀምጣለች፡፡ እርሷ እቴ ወደ አውሮፕላኑ እየገባች ሳይሆን አይቀርም ዕንቅልፍ የጀመራት፡፡ ደግሞ ስፋቷ ለሚኒ ባስ ታክሲ የመጨረሻው ወንበር እንጂ ለአውሮፕላን ወንበር የሚሆን አይደለም፡፡ ከመደገፊያው ተርፎ እኔ ጋ እየመጣ አስቸገረኝ፡፡ ሦስት ትራስ ደራርባ፣ በዚያ ላይ ፎጣ መሳይ ነገር ለብሳ ትለጥጠዋለች፡፡
እኔን መከራ ያሳየኝ ዕንቅልፏ አይደለም፡፡ እየተረፈ የሚመጣው ሰውነቷ አልበቃ ብሎ እንደ ፔንዱለም ስትወዛወዝ ትከሻየ ላይ እየመጣች ዘፍ የምትለው ነገር ነው፡፡ ሴትዮዋ የመጣችው ‹ሶሪ› ከሌለበት ሀገር ነው መሰለኝ ትከሻዬን ገጭታው ስትመለስ ከጥቁሩ ፊቷ መካከል ብልጭ የሚል ባለ ቀይ ድድ ጥርሷን ብቻ አሳይታኝ ‹ካለፈው የቀጠለ› ብላ ወደ ዕንቅልፏ ትገባለች፡፡ ትቆይና ደግሞ ክላሲካል ትለቃለች፡፡ ‹‹ፉርርርርርር›› የሚል የኩርፊያ ክላሲካል፡፡
መቼም በዚህ ክላሲካል ታጅቦ እንኳን ዕንቅልፍ መተኛት ቅዠት መቃዠትም አይቻልምና ከያዝኳቸው መጻሕፍት አንዱን አወጣሁ፡፡ ‹‹የአሲምባ ፍቅር›› የሚል ካሕሣይ አብርሃ በተባለ የኢሕአሠ(የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ሠራዊት) ታጋይ የተጻፈ መጽሐፍ፡፡ መጽሐፉ ከሥነ ጽሑፍ አንጻር ብዙ የሚቀሩት ነገሮች ቢኖሩም የዚያን ዘመን ወጣቶች ታሪክ በማሳየት አንጻር ግን ማራኪ ነው፡፡  መቼም ሰው በአውሮፕላን ሲሄድ አውሮፕላኑ እንዳይወድቅ እንጂ ከአውሮፕላኑ ውስጥ ሰው እንዳይወድቅ የሚሰጋ አይመስለኝም፡፡ እኔ ግን አንድ ገጽም ሳላነብብ በቀኝ ትከሻዬ በኩል የሆነ ነገር ዘፍ አለብኝና ሰጋሁ፡፡ ተጠንቅቄ ዘወር ስል ሴትዮዋ ሳታስፈቅደኝ ትከሻዬን ተንተርሳዋለች፡፡ እንደምንም ታግዬ ሳስለቅቃት ነቅታ ጥርሷን ብልጭ ታደርግና ዕንቅልፏን ከተቋረጠበት ትቀጥላለች፡፡
አሁን ምን ተብሎ ይጸለያል? እኔ እስካሁን በቀኝ ትከሻ በኩል ዘፍ ለምትል ሴት መከላከያ የሚሆን ጸሎት የነገረኝ ሰው የለም፡፡ ከኔ መለስ ሳደርጋት በወዲያኛው በኩል ወደተቀመጠው ፈረንጅ ሄዳ ዘፍ አለች መሰል ‹ኦ ማይ ጎድ› ሲል ሰማሁት፡፡ ‹‹እስኪ ያንተ ጸሎት ከሠራ እኔም እጠቀምበታለሁ›› ብዬ ጠበቅኩት፡፡ ሲብስበት ጊዜ ከወንበሩ ተነሥቶ ወደ መጸዳጃ ቤት አመራ፡፡ የፈረንጅ ነገር፣ ለሁሉም ችግር ወደ መጸዳጃ ቤት ነው፡፡ ‹ከአፍርንጅ የምንለይበት›› የሚለው የ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሀገራችን መጽሐፍ ትዝ አለኝ፡፡   
‹‹የአሲምባ ፍቅር›› የዚያ ዘመን ወጣቶች ለሀገራቸው የነበራቸውን ፍቅር፣ ለነጻነት የነበራቸውን ታጋይነት፣ ላመኑበት ነገር ይከፍሉት የነበረውን መሥዋዕትነት፣ በሌላው ዓለም ያዩትንና ያነበቡትን በሀገራቸው ለማምጣት የነበራቸው ሕልም፣ ለአብዮት የነበራቸውን ጽኑ ፍቅር ያሳያችኋል፡፡ ያንን የመሰለ ትውልድ በጦርነት፣ በእሥርና በግድያ፣ በስደትና በጉስቁልና ማጣት ሀገሪቱን ምን ያህል እንደ ጎዳት ታዩበታላችሁ፡፡ ውጊያና ትግል፣ ስብሰባና ግምገማ፣ ኮንፈረንስና የእርምት ንቅናቄ፣ ተሐድሶና የፖለቲካ ትምህርት፣ ቋንቋው የነበረ አንድ ትውልድ እንዴት እንደጠፋ ትታዘባላችሁ፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የአመራር እጦት፣ የብስለት መጥፋት፣ የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ያላስገባ የትግል ስልት፣ የግለሰብን ነጻነት ያጠፋ ቡድናዊ አምባ ገነንነት፣ ችግሮችን ሁሉ በመሣሪያ አፈሙዝ ለመፍታት የነበረው አመለካከት፣ ራስን በምሁራዊ አምባ ላይ አስቀምጦ ሌላውን የመናቅ አባዜ፣ ከተማ ላይ ተቀምጦ የገጠርን ትግል የመምራት ድንግርግር፣ በሀገሪቱ ትውልድ ላይ ያመጣውን ምስቅልቅልም ታያላችሁ፡፡
እነዚህን መሰል መጻሕፍት ሳነብ እጅግ የሚገርመኝ ነገር ያ ትውልድ ፈጽሟቸዋል ብለን የምናስባቸው ስሕተቶች ዛሬም እንደገና እየተመላለሱ መፈጸማቸው ነው፡፡ አሁንም ችግሮችን በኃይል ለመፍታት ስንሞክር፣ አሁንም ድርጅቶች፣ ማኅበራት፣ ፓርቲዎች ከግለሰብ ነጻነት በላይ ሲሆኑ፣ አሁን የፓርቲ መሪዎች ችግሮችን በመከፋፈልና በመለያየት ሲፈቱ፣ አሁንም ሕዝብና ፀረ ሕዝብ፣ አንድነትና ፀረ አንድነት፣ አብዮታዊና ሊበራል፣ ኮሙኒስትና ካፒታሊስት የመከፋፈያ መሣሪያዎቻችን ሲሆኑ፣ አሁንም በጠላት መቃብር ላይ ሕንጻ የመሥራት አባዜ አልለቀን ሲል፣ አሁንም የተቃራኒያችንን አመለካከት ለማዳመጥ ትዕግሥት ሲያንሰን፣ ምን ያህል ከዚያኛው ዘመን ስሕተት እንዳልተማርን ያሳዩናል፡፡
ተዋጊዎቹ ወጣቶች በአንዳንዶቹ ውጊያዎች አይስማሙም፣ በአንዳንዶቹ ውጊያዎች ደግሞ ከአመራሮቻቸው ተቃራኒ የሆነ መረጃ አላቸው፣ ፓርቲውና ድርጅቱ እየተሳሳተ ያዩታል፣ ስሕተቶቹ የሚያስከፍሉትን ዋጋ በርግጠኛነት እያገኙት ነው፤ ነገሮች እንደማይሁኑ ሲሆኑ እየታዘቡ ነው፤ በተሳሳተ አመራር፣ በተሳሳተ የመፍትሔ ጉዞ፣ በተሳሳተ አሠራር የተነሣ ውድ የሀገሪቱ ልጆች ሕይወታቸውን ከጎናቸው ሲሠው እያዩ ነው፡፡ ነገር ግን ድርጅት፣ ፓርቲ፣ አመራር የሚባሉት ሰዎች አይሳሳቱም፣ እነርሱ ያሉት ሁሉ ቅዱስ ነው፣ እኔ ካየሁት ያላየው አመራር ይበልጣል፤ እኔ ስሕተት መሆኑን ባውቅም ፓርቲው ትክክል ነው ካለ ትክክል ነው፤ ሁለትና ሁለት ተደምሮ አራት የሚሆነው ፓርቲው ወይም ድርጅቱ አራት ነው ካለ ብቻ ነው፡፡ ያለበለዚያ ግን ሦስትም አምስትም ሊሆን ይችላል ብሎ የማሰብ አባዜ ዋጋ ሲያስከፍል እናያለን፡፡ ዛሬም ግን ይሔው አስተሳሰብ በዚህች ሀገር ውስጥ ሥሩን ተክሎ ቅጠል አውጥቶ፣ አብቦና አፍርቶ እየታየ ነው፡፡ ካለፈው ተምሮ እርሱን ለማረም የሚተጋ አይታይም፡፡
አውሮፕላናችን ሁለት ሰዓት ያህል ዘግይቶ ዱባይ ገባ፡፡ እኔ ዱባይ የገባሁት ቀጣዩን አውሮፕላን ለመያዝ 15 ደቂቃ ብቻ ሲቀረኝ ነው፡፡ ምድር ከወረደ በኋላ የበረራ አስተናጋጆች የተወሰን ሰዎችን ስም ጠርተው ውጭ የአየር መንገዱን ሰዎች እንድናነጋግር አሳሰቡን፡፡ እሺ ብለን ስንወጣ አገኘናቸው፡፡ የሆነች ወረቀት ሰጡንና እንዲህ ያለ ቦታ ሄዳችሁ የሆነ ሰው ታገኛላችሁ ሩጡ አሉን፡፡ መቼም አበበና ማሞ፣ ምሩጽና መሐመድ ከድር፣ ኃይሌና  ቀነኒሳ ከተወለዱበት ሀገር የመጣን ነን ብለን ወደተባለው ቦታ ሮጥን፡፡ ሲዖል ይዘጋላችሁና የነገሩን ቦታ ሁሉ ዝግ ነው፡፡ አንዳች ሰው በአካባቢው የለበትም፡፡ ‹አይ አየር መንገዳችን፤ እነ ክበበው ገዳ የት ሄደው ነው እርሱ እንዲህ ያለ ቀልድ የሚቀልደው› ብዬ ተገረምኩ፡፡ ማንን እናናግር፡፡ በኋላ አንድ የአውሮፕላን ማረፊያውን ፖሊስ አገኘነውና ችግራችንን ስንነግረው በፍተሻ ማለፊያው በኩል አድርጎ ወደ ምድር ቤት ወሰደን፡፡
 ምድር ቤት ወርደን የኢትዮጵያ አየር መንገድ መስኮት ስንደርስ እነርሱ ምን አለባቸው አራት ሆነው ቁጭ ብለዋል፡፡ ‹‹ምናለ አንዳችሁ እንኳን እዚያ ተገኝታችሁ ብትረዱን›› አልኳቸው፡፡ ‹‹እገሊትኮ ነበረች›› አሉን፡፡ ትኬታችንን ተቀብለው አየት አደረጉና ‹‹አሁንማ ረፍዷል ቀጣይ አውሮፕላን ካለ እንይላችሁ›› አሉን፡፡ ለእነርሱ እየተባበሩን ነው፡፡ ስሕተቱን የፈጸሙት እነርሱ፣ የዘገዩት እነርሱ የምንቀጣው እኛ፡፡ እንዴው ግን እስከ መቼ ነው የኢትዮጵያ አየር መንገድና የደንበኞቹ ግንኙነት የባላባትና የጢሰኛ የሚሆነው? በባላባቶች ፍርድ ‹‹ምን ባላባት ቢያጠፋ ጢሰኛ ይክሳል›› ይባላል፡፡ አየር መንገዳችንም እንዲህ ሆነብንኮ፡፡ ‹‹ይቅርታ፣ እስኪ ዐረፍ በሉ፣ ችግሩን እንፈታዋለን›› ከአማርኛችን ውስጥ የሌሉ ይመስል ምነው ከአንደበታቸው አልወጣ አሉ?
‹‹እናንተ ባጠፋችሁ ቁጥር እኛ መቀጣት አለብን?›› አልኳቸው ኃላፊ የመሰሉትን ሴትዮ፡፡ምንም አልመሰላቸውም፡፡ ከሌላው አየር መንገድ ጋር በስልክ ተነጋገሩ፡፡ ደግነቱ ያኛው አውሮፕላን አርፍዷል፡፡ ‹‹ትደርሳላችሁ ሂዱ አሉን፡፡›› ሄድን፡፡ እንደተባለውም ደረስን፡፡ ዛሬ ከአየር መንገዳችን ጋር የሚወዳደሩም የሚፎካከሩም አየር መንገዶች በበዙበት ጊዜ እንዲህ በደንበኞች አገልግሎት ላይ መቀለድ ምን ሊያመጣ እንደሚችል ለአየር መንገዳችን ኃላፊዎች ደጋግሞ ማሳሰብ ይገባል፡፡ የያዛችሁት አየር መንገድ ‹የኢትዮጵያ› ነው፡፡ የእናንተ አይደለም፡፡ እናንተ በምትፈጥሩት ስሕተት ግን የምትቀጣው ኢትዮጵያ ናት፡፡ ዛሬ እነ አልጀዚራ ስለ ኢትዮጵያ የሚወራ ክፉ ነገር ፍለጋ አሰፍስፈው በሚጠብቁበት ዘመን እናንተ ተባባሪ ሆናችሁ ክፉ ዜና የምትሰጡበትን ምክንያት እንኳን እኛ እናንተም የምታውቁት አልመሰለኝም፡፡
አሁን ከዱባይ ወደ ብሩናይ ለመጓዝ በሮያል ብሩናይ አውሮፕላን የመንገደኞች ማስተናገጃ ክፍል እገኛለሁ፡፡ ‹‹ባለቤት ያቃለለውን አሞሌ ባለ ዕዳ አይቀበለውም›› ይባል ነበር፡፡ እዚህ ግን ፉርሽ ተደረገ፡፡ አየር መንገዳችን ያቃለለንን መንገደኞች የብሩናይ አየር መንገድ ሰዎች ጋብዘውና ተከባክበው ካሱን፡፡ ‹‹ብሩናይ የሚባል ስም ከዚህ ጉዞ በፊት ሰምቼ አላውቅም፡፡ በዙሪያየ የተቀመጡት እስያውያን ናቸው፡፡ ሰውነታቸው ቀጨጭ፣ ዓይናቸው ሰለምለም፣ ልብሳቸው ደመቅመቅ፣ ፀጉራቸው ወረድረድ ያሉ ሕዝቦች፡፡ በአካባቢው ያለሁት አፍሪካዊ እኔ ብቻ ነኝ፡፡ ከዐርባ ደቂቃ በኋላ እንነሣለን ተብሏል፡፡ እስኪ ቀጣዩን መንገድ ደግሞ ሰላም ያድርገው፡፡
ዱባይ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ዐረብ ኤምሬት  

የዛሬ ሃያ ዓመት ከኮተቤ መምህራን ኮሌጅ እንደተመረቅኩ የመምህርነት ሥራዬን የጀመርኩት እነዋሪ በምትባል በሰሜን ሸዋ ውስጥ ከምትገኛና ከአዲስ አበባ 165 ኪሎ ሜትር በምትርቅ ከተማ ውስጥ በሚገኝ ትምህርት ቤት ነበር፡፡ እነዋሪ ከመርሐቤቴ እስከ ዜና ማርቆስ የሚኖረው ቆለኛና ደገኛው ጅሩዬ የሚገናኙባት የቀለጠች የገበያ ከተማ ናት፡፡ በተለይም በፍራፍሬ ምርቷ ትታወቃለች፡፡ ኤፍሬም እሸቴ የእነዋሪን ሙዝ ‹ከማጠሯ መጎጠሯ› እያለ ይቀልድባት ነበር፡፡
ከእነዋሪ እየተነሣሁ እስከ ዠማ ወንዝ ድረስ ለሠርግም፣ ለንግሥም ቆላውን እወርድ ነበር፡፡ ገበሬዎቹ ከቆላው ይመጡና እኔን በቅሎ ላይ አውጥተው በትከሻቸው ላይ ውጅግራ ጠበንዣቸውን ደልደል አድርገው ተሸክመው የጋቢያቸውን ግማሽ ጠቅልለው አናታቸው ላይ በማስቀመጥ፣ ከግራና ከቀኝ በቅሎዋን እየነዱ፣ ያንን እንደ ያሬድ መዝሙር በጆሮ የሚንቆረቆረውን ወጋቸውን እያወጉ፣ እንደ ዝንጀሮ ገደሉን በኩራት ይወርዱታል፡፡ ተረታቸው፣ ቀረርቷቸው፣ ፉከራቸው፣ ዘፈናቸው፣ የታሪክ ትረካቸው፣ ስለ ጀግኖቻቸው የሚገጥሙት ግጥም አሁንም በጆሮዬ እንደ መስክ ነፋስ ሲያልፍ ይሰማኛል፡፡ 

አንድ ቀን ታድያ አይዋ ሰጥ አርጌ የሚባሉ ቆፍጣና ገበሬ አብረውን ወደ ዠማ ሲጓዙ ታች በሌ ስለሚባል ሽፍታ አወጉኝ፡፡ ታች በሌ በተለይ በሞረቶች ዘንድ በጣም የታወቀ አስቂኝ ሽፍታ ነው፡፡ አንድ ሰው ያላሰበበትን፣ ያልተዘጋጀበትንና ያለ ዐቅሙ የሆነውን ነገር ጀመረ ሲባል ዠማዎች ‹‹ምን የእርሱ ነገርኮ የታች በሌ ሽፍትነት ነው›› ይሉታል፡፡ አንድ ሰው በስሜት ብቻ ተነሣስቶ እንዴው የጀብደኛነትን ሥራ ሲሠራ፣ አንድን ነገር አስቦ ከመሥራት ይልቅ ከሠራ በኋላ ሲያስብ ዠማዎች እንዲሁ ‹ታች በሌ› ይሉታል፡፡ ለምን?
ታች በሌ የዠማ ሰው ነው፡፡ የኖረው ከዛሬ ሁለት መቶ ዓመት በፊት በሸዋው አስፋ ወሰን ዘመን ነው  አሉ፡፡ በዚያ ዘመን ሞረትን ይገዙት የነበሩት ጥዱ የተባሉ ኃይለኛ በላባት ነበሩ፡፡ እንዲያውም ጥዱና አስፋ ወሰን እርስ በርሳቸው የሚፎካከሩም የሚፈታተኑም ኃይለኞች ስለነበሩ ግጥሞቻቸው ዘመን ተሻግረው ደርሰውናል፡፡ አስፋ ወሰን ሞረትን ማስገበር ስለፈለጉ
ለሞፈር ለቀንበር የሚሆነኝን
ሳልቆርጠው አልቀርም ዘንድሮ ጥዱን፤
ብለው ለአዝማሪ ነገሩ አሉ፡፡ ይህን የሰሙት ጥዱም
አስፋ ወሰን ይፋት ጠንክረው ይረሱ
ሞረት ጥዷል ብለው ከሚመላለሱ፤
ብለው መለሱላቸው ይባላል፡፡
ጥዱ ኃይለኛ አስገባሪ፣ አስጨንቆ ገዥ ነበሩና ብዙ ገበሬዎችን እንደ ሰም አቅልጠው፣ እንደ ብረት ቀጥቅጠው፣ እንደ ጫማ ረግጠው ይገዙ ነበር፡፡ ከተገዥዎቹ ገበሬዎች አንዱ የነበረው ታች በሌ መረረው፡፡ በልጅነቱ በሰሜን ሸዋ በረሃዎችና ጫካዎች ሸፍተው ገዥዎችን ስላስጨነቁ ሽፍቶች እየሰማ ነበርና ያደገው መሸፈት አማረው፡፡ አንድ ቀን ከብት ይጠብቁ ለነበሩ እረኞች መሸፈቱን ነግሮ የአጎቱን ቁመህ ጠብቀኝ መንትፎ ሸፈተ፡፡ ሸፍቶም ጫካ ገባ፡፡ አገሩም ‹ታች በሌ ሸፈተ› እያለ ከሚዳ እስከ እነዋሪ አወጋ፡፡ አንዳንዱ አደነቀ፤ ዘፈነለት፤ አንዳንዱ ተጠራጠረ፣ አንገቱን ነቀነቀበት፡፡ ‹በምን ልቡ ነው የሸፈተው›› ያሉም ነበሩ፡፡ ጥዱም እገለዋለሁ ብለዋል ተባለ፡፡
ታች በሌ ዠማ ወንዝ በረሃ ውስጥ ወርዶ አንድ ጫካ ውስጥ ተቀመጠ፡፡ መጀመሪያ ስሙ በድፍን ሸዋ ሲገንን፣ ስሙ በየሠርግ ቤቱና በየድግስ ቤቱ የዘፈን መቋጠሪያ ሲሆን እየታየው ልቡ በደስታ ሞቆ ነበር፡፡ ዋል አደር ሲል ግን ታች በሌን ጥያቄዎች ጭንቅላቱን እየሞሉ ያስጨንቁት ነበር፡፡ ለመሆኑ በቂ ስንቅ ይዘሃል? የሸፈትከውኮ በጀግናው ጥዱ ላይ ነው፤ ለመሆኑ በቂ ጥይት ታጥቀሃል? ለመሆኑ ቢመጡብህ የምትሸሽበት የማምለጫ ስርጥ መርጠሃል? አንተ መንደርህ እያለህ አንድ ቆቅ እንኳን አድነህ የማታውቅ እንዴት ጥዱን ለመዋጋት ጫካ ገባህ? ለመሆኑ ዛሬ የታጠቅከውን ቁመህ ጠብቀኝ ተኩሰህበት ታውቃለህ? ቢበላሽ ማን ይጠግንልሃል? ከዛሬ በፊት ለመሆኑ ጫካ ውለህ አድረህ ታውቃለህ? ከአውሬ ጋር ታግለህ ታውቃለህ?
እነዚህ ጥያቄዎች ጭንቅላቱን ሲወጥሩት ታች በሌ መልስ አልነበረውም፡፡ የዠማን በረሃ ወደ መርሐ ቤቴ ሲያልፍበትና ወደ ጅሩ ሲወጣበት እንጂ ውስጡ ገብቶ ሥር ማንሥሩን አይቶት አያውቅም፡፡ እንዲያውም አሁን ሲያስበው ትንሽ ፍርሃት ሳይኖርበት አይቀርም፡፤ እንደ ሌሎቹ እንኳን ቅራት (ከብትን በረሃ ውስጥ ሌሊት መጠበቅ) ለብቻው አድሮ አያውቅም፡፡ ደግሞ አሁን ሸፍቷልና የሚያወያየው እንኳን የለም፡፡ እየዋለ እያደረ ሃሳብ ሲበዛበት ታች በሌ ይጨንቀው ነበር፡፡ ሽፍትነት ሲያስቡትና ሲሸፍቱት አንድ አልሆነለትም፡፡ እርሱ እዚህ በረሃ ውስጥ ምን እንደሚያደርግ ጨንቆታል፣ እዚያ መንደር ውስጥ ግን በስሙ ይዘፈን ይሆናል፡፡ የልቡን ማን አየለት፡፡ ለእርሱ ከሚዘፍኑለት ስንቅና ትጥቅ ቢያቀብሉት ነበር የሚሻለው፡፡
ታች በሌ ለአንድ ሳምንት በረሃው ውስጥ ተቀመጠ፡፡ ስንቅና እድሜ እያደር ይቀላል እንዲሉ የያዘው ነገር ሁሉ እያደር ያልቅበት፣ እርሱም ብቸኛነትን አልለመደውም ነበርና እያደር ሆድ ይብሰው ጀመር፡፡ አንዳንዴም ሲያስበው መሸፈት እንዳልነበረበት ራሱን ይሞግታል፡፡ አሁን እንዴት አድርጎ ወደፊት መጓዝ እንደሚችል ያስባል፤ ግን ምንም ሃሳብ ሊመጣለት አልቻለም፡፡ ወደ ኋላ እንዳይመለስ ሰው ምን ይለዋል? አንዳንዴ የተወለደበትን ቀን ትቶ የሸፈተበትን ቀን ይረግማል፤ አንዳንዴ ደግሞ እንኳን ሸፈትኩ ይላል፡፡ ቢጠብቅ ቢጠብቅ ጥዱም ሆኑ የጥዱ አንጋቾች ወደ አካባቢው ዝር ሊሉ አልቻሉም፤ ታድያ ሳይዋጋ ሽፍታ ተብሎ እስከ መቼ ሊቀመጥ ነው፡፡ እንዲህ ከሆነኮ ጥቂት ቆይቶ ይረሳል፡፡
ታች በሌ እየቆየ ነገር ዓለሙ መረረው፤ መሸፈቱንን እንጂ ለምንና ምን ሊያደርግ እንደሸፈተ ለኅሊናው ማስረዳት አልቻለም፤ ቀጥሎ ምን እንደሚያደርግና ከዚያስ መጨረሻው ምን እንደሆነ ሊያውቀው አልቻለም፡፡ እገሌ ሸፈተ ሲባል እንጂ ሽፍትነት ምን እንደሆነ፣ ሸፍቶ ምን እንደሚደረግ በልቡ ምንም ነገር አልያዘም፡፡
አንድ ቀን ታች በሌ ድንገት የሚኖርበት መንደር ያለች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በቅዳሴ ሰዓት ከች አለ፡፡ አገርም ጉድ አለ፡፡ ካህናቱም ጨዋውም እያየው አፉን ይዞ ቀረ፡፡ ታምር ተሰምቶ የሰንበት ቂጣ ሊታደል ሲል ታች በሌ ድንጋይ ይዞ ሕዝቡ እግር ሥር ወደቀና ይቅርታ ጠየቀ፡፡ ሰይጣን አሳስቶኝ ነው ብሎ በዚያ መከረኛ ላይ አላክኮ ካህናቱ ድንጋዩን አነሡለት፡፡
አንድ ሰሞን የታች በሌ ነገር የሞረቴ ሁሉ አፍ ማሟሻ ሆነ፡፡ ከዚያ በኋላ ለሞረቴ መሸፈት ቀላል አልሆነም፤ ‹‹ደግሞ እንደ ታች በሌ ሲርብህ እንዳትመጣ›› የሚባለው ብዙ ነው፡፡ እንዲያውም አንድ ሰው ሸፈተ ሲባል አቅራሪዎቹ
ምከሩት፣
ምከሩት፣
ምከሩት፣
ይህንን ታች በሌ ለምን አትመክሩትም፤
ይህንን ታች በሌ ለምን አትነግሩትም፤
ልብ ካልሸፈተ እግር አይሸፍትም ….. ሃ!
እያሉ ይመክሩት ነበር፡፡ ታች በሌ ሳያስቡ ለሚወስኑና ሳያስቡ ለሚያደርጉ ሁሉ የሚሰጥ ቅጽል ሆነ፡፡
ታች በሌያዊ አስተሳሰብ የሀገራችን ተቋማት አንዱ ችግር ነው፡፡ አንዳንድ ፓርቲዎች፣ ማኅበራት፣ ድርጅቶች፣ ኩባንያዎችና ስብስቦች ሳይታሰቡ ተመሥርተው ሃሳብ የጠፋባቸው ናቸው፡፡ ለሃሳብ ተቋም ከመመሥረት ይልቅ ለተቋማቱ ነው ሃሳብ እየተፈለገ ያለው፡፡ ቁጭት ሁሉ፣ ብስጭት ሁሉ፣ ስብስብ ሁሉ፣ ገንዘብ ሁሉ፣ አጋጣሚ ሁሉ ድርጅት፣ ፓርቲ፣ ተቋም፣ ማኅበር ለመመሥረት መዋል የለበትም፡፡ እነ ዕገሌ ስለ መሠረቱ፣ እነ እገሌ ስለተሰባሰቡ፣ የዕገሌ አካባቢ ሰዎች በስማቸው ፓርቲ ስለመሠረቱ፣ የዚህ ዓይነት ሞያ ሰዎች ማኅበር ስላቋቀቋሙ፣ የዚያ ሀገር ሰዎች ኮሙኒቲ ስለ ፈጠሩ፣ እንቶኔና እንቶኔ ኩባንያ ስላቋቋሙ እኛም ማቋቋም የለብን፡፡  
መጀመሪያ ሃሳብ ይቅደም፡፡ ማሰብ ማለት ደግሞ ሃሳብን ብልጭ ማድረግ ማለት አይደለም፡፡ ይህማ ታች በሌን መሆን ነው፡፡ ብልጭ ያለውን፣ ቁጭት የፈጠረውን ሁሉ ሳያስቡበት ተጣድፎ ማድረግ፡፡ ማሰብ እንዲህ አይደለም፤ ግራ ቀኝ የታሰበበት፣ የተጠናና የተነበበበት፣ ከቀደምቶች ልምድ የተቀሰመበት፣ ከተሳካላቸውም ካልተሳካላቸውም ትምህርት የተወሰደበት፣ እንዴት እንደሚኬድ፣ ግቡ ምን እንደሆነ፣ የተሻለው መንገድ የትኛው እንደሆነ፣ የሚያስፈልጉ ነገሮች ምን እንደሆኑ፣ ከነ ማን ጋር መተባበር እንደሚገባ፣ ምን ሊያጋጥም እንደሚችል፤የፍልስፍና መስፈንጠሪያው ምን እንደሆነ አጥልቆና አልቆ መመርመር ነው- ማሰብ፡፡
አንዳንድ ሰው አስቤያለሁ ሲል ‹‹ይህ ነገር በአእምሮዬ መጥቶልኛል›› ማለቱ ነው፡፡ ይህኮ ሰው በመሆኑ ብቻ የሚያጋጥመው ነው፡፡ በአምስቱ የስሜት ሕዋሳቱ መረጃዎች ወደ አእምሮው ሲገቡ ልክ በቁልፍ እንደሚነሣ መኪና ቅንጭሌውን ሊያስነሡት ይችሉ ይሆናል፡፡ ይህ ግን መኪናው በቁልፉ ስለተነሣ ብቻ ሄደ እንደማይባለው ሁሉ ሰውዬውም አሰበ አያስብለውም፡፡ መጀመሪያ የመኪናው ባትሪ ቀጥሎ ሞተሩ መነሣት አለበት፡፡ ሞተሩ ደግሞ ሌሎችን ሁሉ አንቀሳቅሶ ሙሉ መኪናው መሥራት አለበት፡፡ ያን ጊዜ መኪናው ሄደ ይባላል፡፡
ሰውም ሃሳብ ብልጭ ስላለለት፣ የሆነ ቁጭት ስለተፈጠረበት፣ ከሆነ ሰው አንዳች ነገር ስላገኝ፣ በአጋጣሚ አንድ መረጃ ስለደረሰው፣ ቅናት ስላደረበት፣ ዕድል ስለተፈጠረለት፣ ዘመዶቹ ክፈት እንረዳሃለን ስላሉት ብቻ ተቋም፣ ድርጅት፣ ፓርቲ፣ ማኅበር መመሥረት የለበትም፡፡ አንዳንዶች የሆነ ነገር ለማድረግ አስበው ከመሰባሰብ ይልቅ ተሰባስበው ምን እንናድርግ? ብለው ያስባሉ፡፡ አንዳንድ ፓርቲዎች እንደ ታች በሌ ሳያስቡ የሸፈቱ ናቸው፡፡ የተለየ ሃሳብ፣ የተለየ ፍልስፍና፣ የተለየ አቋም፣ የተለየ መንገድ ሳይኖራቸው እንዴው በፓርቲዎቻችን ቁጥር ላይ አንድ ለመጨመር ያህል ብቻ የተመሠረቱ፡፡ ፓርቲው ከተመሠረተ በኋላ ነው ፕሮግራም፣ መመሪያ፣ ፍልስፍና፣ መንገድ፣ የሚያዘጋጁት፡፡ በሃሳብ ስለማይመሠረቱ ከተመሠረቱ በኋላ በሃሳብ ይለያያሉ፡፡ ሳስበው እንዲያውም ለሁሉም ችግሮቻችን መፍትሔ ስጡ ስንባል ኮሚቴ ማቋቋም የሚቀናን ለማሰብ ጊዜ ስለማንሰጥ ይመስለኛል፡፡ የስብሰባ፣ሞቅታ የፈጠራቸው ኮሚቴዎች ሃሳብ አጥተው ሲላጉ አባሎቻቸውን አንጠባጥበው መቼ እንደፈረሱ እንኳን ሳይታወቅላቸው ይፈርሳሉ፡፡ ታች በሌዎች በቁጭት ብቻ ተነሥተው የመሠረቷቸው የሞያ ማኅበራትም ከዓመታዊ ጉባኤ ያለፈ ሃሳብ ሊመጣላቸው ስላልቻለ፡፡ በአንድ ሊቀ መንበር ሃያ ዓመት እያዘገሙ እንዴት ናችሁ? ሲባሉ ‹አለን›› እያሉ ካሉት በታች ከሞቱት በላይ ሆነው ይኖራሉ፡፡
አንዳንዶችም አሉ፤ ምን እንደሚጽፉ ሳያስቡ መጽሐፍ ለመጻፍ የሚነሡ፡፡ ምን እንደሚገጥሙ ሳያስቡ ግጥም ለማሳተም የሚውተረተሩ፡፡ ምን እንደሚያቀርቡ ሳያስቡ ፊልም ለማዘጋጀት ገንዘብ የሚያሰባስቡ፡፡ የተለየ ሃሳብ ሳይኖራቸው የሬዲዮ የዐየር ሰዓት የሚገዙ፡፡ ምን እንደሚጠይቁ ሳያስቡ የቃለ መጠይቅ ማይካቸውን ተጠያቂው ላይ የሚተክሉ ቀልደኞች፡፡ ለነገሩ በሠፈር አንድ ሱቅ ሲከፈት የሠፈሩ  ሰው ሁሉ አጥሩን እየቀደደ ሱቅ መሥራት የተለመደበት ሀገር ውስጥ ነው ያለነው፡፡ ያዋጣል ወይ? ከጎረቤቴ በምን እለያለሁ? እኔ ምን አዲስ ነገር አመጣለሁ? ብሎ ሳያስብ ነው ሱቁን ቦግ የሚያደርገው፡፡ ሱቁን ከሠራና ዕቃ ካስገባ በኋላ ነው ማሰብ የሚጀምረው፡፡ ይህ ነገር ወደ ተቋሞቻችንም ተጋብቷል፡፡ ምን ተቋሞቻችን ብቻ ትዳሮቻችንም እንዲህ እየሆኑኮ ነው፡፡ ማግባት የሚፈልግ እንጂ እንዴትና ለምን እንደሚያገባ፣ የጋብቻው ጠባይና አካሄድ ምን እንደሚመስል አስቀድሞ የሚያስብ ጥቂቱ ነው፡፡  የሆነ ቦታ ለመሄድ እያሰብኩ ነው፤ የሆነ ነገር ሳልከፍት አልቀርም፤ አንድ የሆነ መጽሐፍ ልጽፍ እያሰብኩ ነው፤ የሚላችሁ ሰው ሳያስብ አንዳች ነገር ሊያደርግ የተዘጋጀ መሆን አለበት፡፡
አስቦ መሥራት እንጂ ሠርቶ ማሰብ ኪሣራው ብዙ ነው፡፡ ገበያ መውጣታቸውን እንጂ ምን ሊገዙ እንደወጡ፣ ቤት መሥራትና መግዛት እንጂ ምን ዓይነት ቤት እንደሚገዙ ወይም እንደሚሠሩ፣ ውጭ ሀገር መሄድ እንጂ ለምንና እንዴት እንደሚሄዱ፣ የማያስቡ አሉ፡፡ በአንዳንድ ሀገሮች የነበረውን መንግሥት ስለመቀየር እንጂ በቅያሪው ስለሚመጣው መንግሥት ስላልታሰበበት የመጣው ከሄደው የባሰበት ጊዜ አለ፡፡ ለዚህ ነው ታች በሌያዊ የሆነውን መንገድ ትትን ሃሳብ ከተቋም ይቅደም የምለው፡፡ ሃሳብ ከድርጊት ይቅደም፡፡ ሃሳብ ከመመሪያም፣ ከዐዋጅም፣ ከማፍረስም፣ ከመሥራትም፣ ከመሸለምም፣ ከመቅጣትም፣ ከመሄድም ከመምጣትም ይቅደም ፡፡
አንድ ሰው እንዲያውም ይህንን ነግሮኛል፡፡ የአንድ ገበሬ ውሻ ሁልጊዜ መንገድ ዳር እየቆመ አላፊ አግዳሚውን መኪና ለመያዝ እየተከተለ ይጮኻል፡፡ የገበሬው ጓደኛ ይኼ የውሻው ጠባይ ይገርመዋል፡፡ አንድ ቀን ገበሬውን ‹‹ለመሆኑ ይኼ ውሻህ መኪናውን ተከትዬ እይዘዋለሁ ብሎ ነው እንዲህ መከራን የሚያየው?›› ይለዋል፡፡ ገበሬውም ሳቅ ብሎ ‹‹እኔ ለመያዝ መታገሉ አይደለም የሚያስገርመኝ፤ የሆነ ቀን ሊይዘው ይችላል፡፡ እኔን የሚገርመኝ መኪናውን ቢይዘው ምን እንደሚያደርገው ውሻው አለማሰቡ ነው›› አለው ይባላል፡፡ ታች በሌያዊ  አስተሳሰብ ማለት ይህ አይደለም ታዲያ፡፡

ሁለተኛው ጉዳይ
(ባለፈው ሳምንት ከወላጆች ጋር በሁለት ጉዳዮች ለመነጋገር ተነሥቼ ነበር፤ የመጀመሪያውን ሳምንት አቅርቤአለሁ፤ በየቦታው መወያያ መሆኑን ፍንጭ አግኝቻለሁ፤ እስኪ ሁለተኛውን ዛሬ ላቅርብ)
አንዲት እኅት እንዲህ አወጋችኝ
ለዶክትሬት ጥናቷ ከአሜሪካ ትመጣና አጎቷ ቤት ታርፋለች፡፡ አጎቷ ‹አላቸው› ከሚባሉት የከተማችን ባለ ሀብቶች አንዱ ነበር፡፡ ሁለት ወንዶች ልጆች አሉት፡፡ ልጆቹ የሰባትና የዐሥር ዓመት ልጆች ናቸው፡፡ ልጆቹ በተደጋጋሚ ይታመማሉ፡፡ በሳምንት ቢያንስ አንድ ጊዜ ከሐኪም ቤት አይጠፉም፡፡ ‹‹አንድ ጊዜ እኔ ምሳ ስበላ ልጆቹን ጠራኋቸውና አብረን እንድንበላ ጋበዝኳቸው፡፡ እንጀራ እንደማይበሉ ነገሩኝ፡፡ ምንድን ነው ታዲያ የምትበሉት? አልኳቸው፡፡ ከሱፐር ማርኬት የሚገዛ አንድ የምግብ ዓይነት ነገሩኝ፡፡ ሞግዚታቸውም ያንን ይዛላቸው መጣች፡፡ በዚያ ጊዜ አንዳች ነገር ከነከነኝና ምሳዬን ከጨረስኩ በኋላ ወደ ማዕድ ቤቱ ገብቼ ሞግዚቷን ጠየቅኳት፡፡ ምንድን ነው እነዚህ ልጆች አዘውትረው የሚበሉት? እስኪ አሳይኝ? አልኳት፡፡ መደርደሪያውን ስትከፍተው ሁሉም ከሱፐር ማርኬት የሚገዙ የተፈበረኩ ምግቦች ናቸው፡፡ እጅግ በጣም ገረመኝ፡፡ 

በቀጣዩ ቀን ከልጆቹ ጋር ብስክሌትና ኳስ አብሬ ተጫወትኩ፡፡ ብዙ ጊዜ ወላጆቻቸውን ስለማያገኙ ከእኔ ጋር በመጨዋታቸው ደስ አላቸው፡፡ ከሰዓትም አብሬያቸው እንድጫወት ለመኑኝ፡፡ እኔም ይህንን አጋጣሚ ተጠቅሜ ከእኔ ጋር አብረው ምሳ ከበሉ ብቻ እንደምጫወት ነገርኳቸው፡፡ ቅር እያላቸው ለጨዋታው ሲሉ ተስማሙ፡፡ ቋቅ እያላቸውም በምሳ ሰዓት እንጀራውን በወጥ አብረውኝ በሉ፡፡ ቃል እንደገባሁትም አብሬያቸው ተጫወትኩ፡፡ በቀጣዩ ቀን ከባልትና ቤት የገንፎ እህል ገዝቼ መጣሁ፡፡ ከዚያም ገንፎ ሠራሁና አብረን እንድንበላ ጋበዝኳቸው፡፡ እንደምንም በሉልኝ፡፡ ቆሎ የሚባለውን ነገርማ ነክተውት ቀርቶ አይተውት አያውቁም፡፡ እኔ ግን ቆሎ ለጥርሳቸው ጥንካሬ እንደሚጠቅም፤ ኳስ ተጫዋች መሆን ከፈለጉ ደግሞ መጠንከር እንዳለባቸው፤ ለዚህም ከልዩ ልዩ ጥራጥሬ የተሠራው ቆሎ እንደሚጠቅም ነገርኳቸው፡፡ አብሬያቸው እየተጫወትኩ ስለምነግራቸው ተቀበሉኝ፡፡
በመጀመሪያው ቀን ለጥርሳቸው እንዳይከብዳቸው ለዘዝ ያለ ቆሎ እንዲበሉ አደረግኩ፡፡ ኳስ እንጫወትና በዕረፍት ሰዓት ቆሎ በልተን ውኃ እንጠጣለን፡፡ የተሰጠውን ያህል ያልበላ ይቀጣል እያልን ጨዋታ አደረግነው፡፡ ቂጣውንም በዚህ መልክ ነበር ያስለመድኳቸው፡፡ ማር የተቀባ ቂጣ መብላት አልለመዱም፡፡ ብስክሌት ለመንዳት ግን ቂጣ አስፈላጊ መሆኑን ነገርኳቸውና በብስክሌታቸው ጭኜ ስንነዳ እንበላ ነበር፡፡
እንዲህ እያደረግኩ ሰምተዋቸውም ተመግበዋቸውም የማያውቋቸውን ምግቦች አስለመድኳቸው፡፡ የሚገርምህ ነገር በየሳምንቱ ሐኪም ቤት መሄዱ ቀረ፡፡ ለካስ የእነዚህ ልጆች ችግር የምግብ ችግር ነበር፡፡ ከሱፐር ማርኬት የሚመጡ ምግቦችን እንጂ በባህላችን የሚዘጋጁና ለልጆች የሚያስፈልጉ ነገሮችን የያዙ ተፈጥሯዊ ምግቦችን አይመገቡም ነበር፡፡ ለካስ ልጆቹ እየበሉ የሚራቡ ነበሩ፡፡
ወላጆቻቸው ገንዘብ አላጡም፤ መግዛት የማይችሉም አይደሉም፡፡ ነገር ግን ልጆቻቸውን የወደዱ የሚመላስቸው፣ ልጆቻቸውንም የተከባከቡ የሚመስላቸው ከየሱፐር ማርኬቱ የሚገዙ የተፈበረኩ ምግቦችን በመግዛት፣ በጣፋጮች በማንበሽበሽ፣ ለልጆቹ ስሜት እንጂ ለልጆቹ ጤንነት የማይጠቅሙ የተፈበረኩ ምግቦችን በመስጠት ነው፡፡ ለእነርሱ ዘመናዊነት ማለት የታሸገ ምግብ ነው፣ ጣፋጭ ምግብ ነው፤ የሚገዛ ምግብ ነው፡፡ ርግጥ ነው ልጆቹ ደስ ይላቸዋል፡፡ ‹‹ማሚ እወድሻለሁ፤ ዳድ እወድሃለሁ›› እያሉ ደስታቸው እንዲጨምር ያደርጉታል፡፡ ደጋግመውም እንዲገዙላቸው የሚፈልጉት ይህንኑ ይሆናል፡፡ እነርሱም ብላ አትብላ ከሚለው ጭቅጭቅ ይድኑ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ልጆቹን እየገደልናቸው ነው፡፡ በሁለት መንገድ፡፡
በአንድ መልኩ ማኅበራዊነትን እናሳጣቸዋለን፡፡ አንድ ልጅ ሀገሩን እንዲወድድ፣ ለሀገሩ እንዲያስብና ማኅበረሰቡን ዐውቆ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ ‹ማኀበር› socialization ያስፈልገዋል፡፡ ከማኅበረሰቡ ጋር መግባባት፣ መላመድና ማኅበረሰቡን መሆን፡፡ ከማኀበሪያ መንገዶች አንዱ ደግሞ አብሮ መብላትና መጠጣት ናቸው፡፡ እነዚህ ልጆች ሠርግ፣ ማኅበር፣ ተዝካር፣ ግብዣ እንዴት ነው የሚቀበሉት?  ነገስ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች እንዴት ነው የሚሠሩት? በሌላም በኩል እዚህ ሀገር የሱፐር ማርኬት ምግቦች በዘላቂነት አይገኙም፡፡ ይቀያየራሉ፡፡ ዛሬ ወደ ሀገር ውስጥ ገብቶ ልጆችህ የለመዱት ምግብ ነገ የለም ትባላለህ፤ ያን ጊዜ ልጆቹን ሌላ ነገር ማስለመድ ችግር ይሆንብሃል፡፡
ምን ይሄ ብቻ፡፡ ብዙ ጊዜ የታሸጉ ምግቦች የሚሠሩባቸው ነገሮች ልጆችን ያቃዥቧቸዋል፡፡ ስሜታውያን አድርገው ዕረፍት አልባ ያደርጓቸዋል፡፡ ያን ጊዜ ልጆቹ ረባሾች፣ ቀዥቃዣዎች፣ የማይሰሙ፣ ቀልበ ቢሶች ተደርገው በወላጆቻቸው፣ በቅርብ ዘመዶቻቸውና በሌላው ማኅበረሰብ እንዲነወሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ይሄም ለልጆቹ ከማኅበረሰቡ ጋር አለመቀላቀል አንዱ ምክንያት ይሆናል፡፡
ሁለተኛው ጉዳት ደግሞ ልጆቹን የቅንጦት ረሃብ ውስጥ መጣሉ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ በምዕራቡ ዓለም ተፈጥሯዊ ምግቦችን መመገብ የሥልጣኔና የጤንነት ምልክቶች ናቸው፡፡ ውድ ምግቦችም ተፈጥሯዊ ምግቦች ናቸው፡፡ እኛ ሀገር እነዚህን ተፈጥሯዊ ምግቦች ብዙ ጊዜ የሚያገኙት ‹ድኾች› ናቸው፡፡ እስኪ ዝም ብለህ እይ በከተሞቻችንኮ የተጠበሰ በቆሎ መብላት፣ ቆሎ መብላት፣ ንፍሮ መብላት እየቀረ ነው፡፡ እነዚህ ምግቦችኮ ያልያዙት የንጥረ ነገር ዓይነት አልነበረም፡፡ ገንፎ እንኳንስ ከምግብ ዝርዝራችን ከአራስ ቤትም እየጠፋ ነው፡፡ እኔ የጃፓኖች ምግብ ቤት ገብቼ ከዶሮ ሥጋ ጋር የተቀቀለ በቆሎ ነበር ያቀረቡልኝ፡፡ አሁን እኛ ሀገር እንግዳ ጠርተህ የተቀቀለ በቆሎ ብታቀርብ ስምህ ነው የሚጠፋው፡፡ አንተ ራስህ ግሪክ ሀገር የተጠበሰ በቆሎ በሰባት ዶላር መግዛትህን ስትናገር ሰምቼሃለሁ፡፡ እኛ ሀገር ግን የተጠበሰ በቆሎ ምብላት የድህነት ምልክት ነው፡፡
ልጆቻችንኮ የተመጣጠነ ምግብ እየተመገቡ አይደለም፡፡ ይህ የሆነው በማጣታችን ምክንያት ብቻ አይደለም፡፡ ርግጥ ነው በምግብ እጥረት የሚጎዱ ሚሊዮን ልጆች አሉን፡፡ እኔ ግን የማወራህ በቅንጦት ረሃብ ውስጥ ስላሉት ልጆች ነው፡፡ ድንች እንደ ልብ በሚገኝበት ሀገር፣ በርካሽ ገዝቶ ቀቅሎ ማብላት ሲቻል እንዴት የታሸገ ድንች ጥብስ እናበላቸዋለን፡፡ እኛ በውድ ዋጋ ገዝተን ከምናበላቸው የታሸገ የድንች ጥብስ ይልቅ እነዚህ መንገድ ዳር የተቀቀለ ድንች ገዝተው (እምቦቲቶ) የሚበሉት ይበልጣሉ፡፡ እነርሱ ጋር ችግሩ ንጽሕናው ነው፡፡ በይዘቱ ግን ትክክለኛውና ጤነኛው የእነርሱ እምቦቲቶ ነው፡፡ ቡላና የገብስ ቂጣ እንደልብ በሚገኝባት ሀገር እየኖርን እንዴት ልጆቻችንን በታሸገ ዱቄት እናሳድጋቸዋለን?
ይኼ ፈጽሞ ልጅን መውደድ ሊሆን አይችልም፡፡ የማይሆኑ ምግቦችን እየመገብን ልጆቻችን በትምህርታቸው ሰነፍ ሆኑ ብለን ደግሞ እናማርራለን፡፡ እኔ ድሮ ድሮ የገጠር ልጅ ለምን ጎበዝ እንደሚሆን አሁን ነው የገባኝ፡፡ ገጠርኮ ልጆች ሁሉንም ዓይነት ምግብ ይበላሉ፡፡ የሚዘሩትንና የሚያበቅሉትን ተወው፡፡ ከጫካ የሚገኙ፣ ጤናማ የሆኑና በንጥረ ነገሮች የበለጸጉ ስንት ምግቦች ነበሩ፡፡ እነዚህ ምግቦች እኔ ሕጻን እያለሁ ከገበያ በቀላሉ እናገኛቸው ነበር፡፡ አሁን እንኳን ከተማ ገጠር መገኘታቸውንም እንጃ፡፡ እነ እንኮይ፣ እነ ሾላ፣ አነ ባምባ፣ እነ ኮሽም፣ እነ ግብጦ፣ የት ሄዱ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምታገኛቸው ከ500 ዓመት በላይ የኖሩት አበውኮ እነዚህን ተፈጥሯዊ ፍራ ፍሬዎች ነበር የሚመገቡት፡፡
የገጠሩም ሰው ዛሬ ዛሬ ሥልጣኔ የሚመስለው ልክ እንደ ከተማው ያለ አመጋገብ ነው፡፡ እነርሱ የሚያወጡት ቅብዐ ኑግ እኛ ከዱባይ ከምናስመጣው ዘይት እንደሚበልጥ ልንነግራቸው ይገባል፡፡ ልጅን መውደድ ማለት የሱፐር ማርኬት ምግብ መመገብ ሳይሆን በአካባቢው የምናገኛቸውን ምግቦች እያፈራረቁ እያመጣጠኑ መመገብ ማለት መሆኑን መንገር አለብን፡፡ ይህ አስተሳሰብ በመዛባቱ የተነሣ ቤተሰቦቻቸው በትክክለኛ መንገድ የሚያሳድጓቸው ልጆች እንኳን እንደ ሌሎቹ የተፈበረኩ ምግቦችን ስላልበሉ እያማረሩ ናቸው፡፡ ምክንያቱም ሬዲዮውና ቴሌቭዥኑ በእነዚህ ምግቦች ማስታወቂያዎች የተሞሉ ናቸዋ፡፡
ሲሆን ሲሆን በየብሔረሰቡ ያሉትን ምግቦች አጥንተን ወደ ሀገራዊው ባህል እንክተታቸው፡፡ አንደኛ በቀላሉ ይገኛሉ፡፡ እኛው ጋ ነዋ የሚበቅሉት፤ ሁለተኛ የተፈጥሮ ናቸው፡፡ ከጎጂ ነገሮች ነጻ ይሆናሉ፡፡ ሦስተኛ አሠራራቸው ቀላል ይሆናል፤ በባህል ተሞክረውና ተፈትነው የወጡ ናቸውና፡፡ እነ ጣልያንኮ ፒዛን ከኤርትራ ነው የወሰዱት፡፡ የትግራይ ሰዎች ቂጣውን በቅቤና በአዋዜ የመብላት የቆየ ባህል ነበራቸው፡፡ ጣልያኖች አዋዜውን በቲማቲም ተኩትና ፒዛን አመጡት፡፡ ዛሬ ልጆቻችን ፒዛ ነው እንጂ ቂጣ አንወድም ሲሉ ዝም እንላቸዋለን፡፡
ባይሆን ባህላዊ ምግቦችን ለልጆች በሚጣፍጣቸውና በሚስባቸው መንገድ እንዴት እናቅርባቸው? ብለን ወላጆች መምከር አለብን፡፡ እንደ ምዕራባውያኑ ልጆቹ ከተጎዱና ለአደጋ ከተጋለጡ በኋላ ጉዳዩ ሀገራዊ ጉዳይ እንደሚሆን ጥርጥር የለኝም፡፡ እንዲያውም ከከተማው ይልቅ የገጠሩ ሕዝብ በባለሞያዎች የሚሰጠውን ሃሳብ እየተቀበለ የልጆቹን አመጋገብ እያስተካከለ መሆኑን አንዳንድ ቦታዎች አይቻለሁ፡፡ ጭብጦውን እንዲቀይሩ አይደለም፡፡ ጭብጦውን ከልዩ ልዩ እህሎች በተፈጨ ዱቄት እንዲሠሩት ነው ያስተማሯቸው፡፡ ካገኙ ትንሽ ወተት እንዲያደርጉበት፣ ከተቻለ ደግሞ ቅቤ እንዲጨምሩበት ነው የሚያስተምሯቸው፡፡ ክክ ወጡን እንዲተውት አይደለም የነገሯቸው፤ ክኩን የአተር ብቻ ከማድረግ የሌሎችንም ጥራጥሬዎች እንዲያደርጉት ነው፡፡ ››
ለእኔ እያብራራችልኝ በሄደች ቁጥር ንዴቷ እየጨመረ መጣ፡፡ ሞያዋም፣ ትምህርቷም ስቧት ብዙ ነገር ታዝባለች፡፡ ነገር ግን ከዘመዶቿ ጋር እንኳን በዚህ ጉዳይ መስማማት አልቻለችልም፡፡
‹‹ምናልባትኮ ወላጆች ልጆቻቸውን ትምህርት ቤት ሲልኩ አልበላም ስለሚሏቸው ይሆናል›› አልኳት፡፡
‹‹ልጆችኮ አልበላም የሚሉት ከብዙ ነገር አንጻር ነው፡፡ የምግቡ አዘገጃጀት፣ የጓደኞቻቸው ተጽዕኖ፣ የመመገቢያው ዕቃ፣ ሌሎችም አብረው መታየት አለባቸው፡፡ እንዲያውም እነዚህ ከሱፐር ማርኬት የሚገዙ ምግቦች ልጆቹን ለሌሎች ምግቦች ማለማመጃ ሊሆኑን ይችላሉ፡፡ ሌሎች ምግቦችን ለሚመገቡ ልጆች እንደ ሽልማት በመስጠት፡፡ በሌላም በኩል ልጆቻችን በራሳቸው እንዲተማመኑ ማስተማርም አለብን፡፡ ማሳመን አለብን፡፡ ራሳቸውን እንዲሆኑ፡፡ ይሄ ባህሌ ነው፤ ይህንን እወዳለሁ እንዲሉ፡፡››
ሃሳቧ እጅግ አብዝቼ እንዳስብ አድርጎኛል፡፡ በተለይም ‹የቅንጦት ረሃብ›› ያለችው ነገር ልክ ነው እያልኩ ከራሴ ጋርም ከቤተሰቤ ጋርም ብዙ ሰዓታት ተነጋግሬበታለሁ፡፡ እስኪ ወላጆች ተነጋገሩበት፡፡ ወቅቱ ትምህርት ቤቶች የተዘጉበት በመሆኑ የልጆቻችንን አመጋገብ ለማስተካከል ምቹ ጊዜ ላይ ነን፡፡  ለመሆኑ በየቤታችን የቅንጦት ረሃብ የለም? በየቤታችን የልጆቻችን አመጋገብ የታሰበበት ነው? ስለምንገዛላቸው እንጂ ስለሚመገቡት ነገር እናስባለን፡፡ እኛ ገዛን፣ ሞግዚቶቻቸውስ ይመግቧቸዋል? እስኪ የሰሞኑ የቤተሰብ አጀንዳ ይኼ ይሁን፡፡

በቀደም በቀለበት መንገድ ላይ በመኪና ስሄድ ከጎናችን አንድ ነጭ ፒክ አፕ መኪና ይጓዝ ነበር፡፡ ዘወር ብዬ ሳየው በሩ ላይ የመሥሪያ ቤቱን ስም ለጥፏል፡፡ ያየሁትን ለማመን ስላቃተኝ በሞባይል ፎቶ አነሣሁት፡፡ የድርጅቱ ስም ግምማአድ (AISA) ይላል፡፡ ምን ሆነው ነው እንዲህ ያለ ክፉ ትርጉም የሚያጋልጥ ስም የሚያወጡት፡፡ ለመሆኑ ድርጅቱ በአማርኛ ሲጠራ ምንድን ነው የሚባለው? ‹ግም ማአድ› ማለትኮ በአማርኛ መልካም ትርጉም የለውም፡፡ አሁን እዚያ የሚሠራ ሰው የት ትሠራለህ ሲባል ‹ግምማአድ እሠራለሁ› ይላል ማለት ነው?

አንዳንድ ድርጅቶች የባለቤቶቹን ወይም የረጅዎችን ፍላጎት ማሳካታቸውን እንጂ በባለቤቶቹ ላይ የሚያመጡት ተጽዕኖ ግምት ውስጥ አይገባም፡፡ ያ ስም ከአካባቢው ባህልና እምነት አንጻር በተጠቃሚውም ሆነ በሠራተኛው ላይ ተጽዕኖ ማድረሱ አይገመገምም፡፡ በአንድ ወቅት ጃፓኖች ያመረቱትን መኪና የሰየሙበት ስም በፈረንሳይኛ ‹ሞት › የሚል ትርጉም በመስጠቱ ምክንያት የነበረውን ክርክር አስታውሰዋለሁ፡፡
ባለፈው ጊዜ በደቡብ ጎንደር በንፋስ መውጫ ከተማ በኩል ስናልፍ ‹ዝሙት በኛ ይብቃ› የሚባል የሸቀጣ ሸቀጥ ሱቅ አየን፡፡ ስሙ ገረመንና ለመጠየቅ ጠጋ አልን፡፡ ሱቁ የተከፈተው ከዚህ በፊት በዝሙት አዳሪነት ይተዳደሩ የነበሩ ሴቶችን ከዚህ ዓይነት ተግባር በማውጣት መሆኑ ተነገረን፡፤ ይሁን ሃሳቡ መልካም ነው፡፤ ነገር ግን አንድ ሰው ምንስ ቢሆን ‹እኔ ዝሙት አዳሪ ነበርኩ› ብሎ በአደባባይ እንዲናገር እንዴት ይደረጋል? የእነዚያ ሴቶች ልጆችስ ‹ዝሙት በኛ ይብቃ ሱቅ የኛ ነው› ብለው በኩራት ይናገራሉ? ሰዎችስ ‹ዝሙት በኛ ይብቃ ሱቅ አጠገብ እንገናኝ› ተባብለው ይቀጣጠራሉ? እዚህ አልጽፈውም እንጂ የአካባቢው ሰዎች ሱቁን የሚጠሩት በሌላ ስም ነው፡፡
እስኪ ለዛሬ ‹ግምመአድ› የሚባለው ተቋም ወዳስታወሰኝ በሀገራችን ለንግድ፣ ለመንግሥታዊና መንግሥታዊ ላልሆኑ ተቋማት ስለሚወጡት ስሞች በተለይም ስለ የአሕጽሮት ስሞች እናውጋ፡፡ በታላላቅ ከተሞቻችን ውስጥ ድርጅትንና ሕንፃን በእንግሊዝኛ አሕጽሮት መሰየም እየተለመደ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ስያሜዎች እንኳን እኛ ተመልካቾቹ ቀርተን ባለቤቱም ቢሆን ለመጥራት የሚቸገርባቸው ዓይነት ናቸው፡፡ ESLPTYGQ ሕንፃ የሚለውን እስኪ ምን ብላችሁ ትጠሩታላችሁ? አንድ ቦታ ደግሞ በአማርኛ ‹ትግድብም› የሚባል ሕንፃ አይቻለሁ፡፡ አሁን ይህንን እንዴት አድርጎ ማስታወስ ይቻላል? በተለይም በሀገራችን አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች የወከሏቸውን ብሔር ብሔረሰቦች ሁሉ ለማካተት ሲጥሩ፣ ከዚያ በኋላ ደግሞ ‹ዴግ› የሚል ሲጨምሩበት ስማቸውን ጠርቶ ከመጨረስ የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን አንብቦ መጨረስ ቀላል ይሆናል፡፡
እንደ ፈረንሳይ ባሉ ባደጉት ሀገሮች ለድርጅቶች ስምን የሚያወጡ የታወቁ ኩባንያዎች አሉ፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች የድርጅት ባለቤቶችን ሀሳብ፣ የስሙን ትርጉም፣ ለመጥራት ቀላል መሆኑንና ከሥነ ምግባር ጋር አለመጋጨቱን በማየት ስም ያወጣሉ፡፡ እኛ ሀገር ግን ብዙ ጊዜ የድርጅቱን ባለቤቶች ወይም የቤተሰቦቻቸውን አለበለዚያም ደግሞ የትውልድ ቦታቸውን ስም የመጀመሪያ ፊደሎች ብቻ በያዙ አሕጽሮቶች የሚጠሩ ድርጅቶችና ሕንጻዎች ናቸው ያሉት፡፡ እነዚህን ስሞች ራሳቸው ባለቤቶቹ ይመስሉኛል የሚሰጧቸው፡፡ እነርሱ የፈለጉትን ማድረጋቸውን እንጂ እኛ ደንበኞቻቸው ይመቸን አይመቸን፣ ይስማማን አይስማማን ግድ የላቸውም፡፡ 
የአሕጽሮት ስሞች እንዲሁ በፈቀደ የመጀመሪያ ስሞችን በመገጣጠም ብቻ የሚወጡ አይደሉም፡፡ የራሳቸው የሆነ መንገድና ሥነ ምግባርም አላቸው፡፡ ባለሞያዎቹ የአሕጽሮት ስሞችን ለሚያወጡ ሰዎች ቢያንስ እነዚህን አራት ነገሮች ግምት ውስጥ እንዲያስገቡ ይመክራሉ፡፡
  • አጭር መሆን፡- የአሕጽሮት ስም ሲወጣ በተቻለ መጠን ለመጻፍም ሆነ ለመጥራት አጭር የሆነ ቢሆን ይመረጣል፡፡ በእንግሊዝኛ ከሆነ ከሦስት እስከ ስድስት ፊደል፣ በአማርኛ ከሆነ ደግሞ ከሦስት እስከ ሰባት ፊደል ቢሆን ይመረጣል፡፡ UNESCO ከእንግሊዝኛው ጅንአድ ከአማርኛው መልካም ምሳሌዎች ናቸው፡፡
  • ለመጥራት ቀላል የሆነ፡- የምንኖረው ኢትዮጵያ ውስጥ በመሆኑ የምናወጣቸው የአሕጽሮት ስሞች ለአንድ ኢትዮጵያዊ ለመጥራት ቀላል የሚሆኑ መሆን አለባቸው፡፡ ከላይ እንዳየነው ESLPTYGQ እንደሚለው ዓይነቱን ስም አንድ ኢትዮጵያዊ እንዴት አድርጎ በቀላሉ ይጠራዋል? ይህንን መሰሎቹን አሕጽሮቶች ባለሞያዎቹ ‹የፊደላት ሾርባ› Alphabet soup ብለው ይጠሯቸዋል፡፡
  • ሌላ ትርጉም የማይሰጡ፡- የምናወጣው አሕጽሮት የባለቤቶቹን ስም መያዙ ብቻ መታየት የለበትም፤ በእንግሊዝኛም ሆነ በአማርኛ ወይም በሌላም ቋንቋ ቢሆን ሌላ ዓይነት ትርጉም የማይሰጥ መሆን አለበት፡፡ ለምሳሌ ‹ግምመአድ› ለአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የመልካም ነገር መገለጫ አይደለም፡፡
  • ልዩ የሆነ(ያልተደገመ) የምንሰጠው አሕጽሮት የራሳችን የሆነና ከዚህ በፊት ያልተደገመ ቢሆን መልካም ነው፡፡ በአንዳንድ ሀገሮች አሕጽሮቶችን የሚመዘግቡ መዛግብት አሉ፡፡ የታወቁ አሕጽሮቶችን የሚይዙ ድረ ገጾችም አሉ፡፡ በመንግሥታዊም  ሆነ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች፣ ብሎም በታወቁ ዓለም አቀፍ ጉዳዮች የታወቁትን አሕጽሮቶች መጠቀም ክርክርና መምታታትን ያስከትላል፡፡
የአሕጽሮት ስሞችን ለድርጅቶቻቸው ማውጣት ለሚፈልጉ አካላት በዓለም ላይ የተሻሉ መንገዶች ተብለው የሚመከሩትን ዘዴዎች ቢከተሉ ያዋጣቸዋል፡፡ ከእነዚህ የአሕጽሮት ማውጫ ዘዴዎች መካከል የሚከተሉት መንገዶች ልንጠቀምባቸው የምንችላቸው ናቸው፡፡
1.   ትርጉም የሚሰጥ ቃል መፍጠር፡- ቃላቱን በማሳጠር አሕጽሮት ስናወጣ በተቻለ መጠን ትርጉም እንዲሰጡ አድርጎ ማውጣት ማለት ነው፡፡ ለዚህ በሀገራችን ምሳሌ የሚሆነን ለረዥም ዘመን የምናውቀው ኩባንያ ‹በርታ› ነው፡፡ በርታ በአንድ በኩል በእንግሊዝኛው ‹ብርሃኔና ታደሰ› የሚባሉት ባለቤቶቹ ስም አሕጽሮት ሲሆን በአማርኛ ደግሞ ‹ጎብዝ፣ ጀግን› ማለት ነው፡፡ አንድ ቦታም ‹ድንበሩና በርይሁን› የተባሉ ጓኛሞች የመሠረቱትን ‹ድንበር› የተባለ ኩባንያ አይቻለሁ፡፡ በእንግሊዝኛም Radar – Radio Detention and Ringing, Interpol- International Police,  በምሳሌነት ይጠቀሳሉ፡፡ ይህንን ዓይነት ስያሜ ለመስጠት የግድ የስሞቹ የመጀመሪያ ፊደሎች ብቻ ሳይሆን ከስሞቹ የተወሰኑትን መውሰድ፣ ወይም አያያዦችንም ማካተት ሊያስፈልግ ይችላል፡፡ MATYAS ሕንፃ በአንድ በኩል የባለቤቶቹ ስሞች አሕጽሮት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ትርጉም ያለውን የሐዋርያ ስም ይሰጣል፡፡
2. የመጀመሪያ ፊደል አሕጽሮት፡- የስሞቹን የመጀመሪያ ፊደል ብቻ በመውሰድ ቢቻል ትርጉም ያለው፣ ባይቻል ለአጠራር ምቹ የሆነ ስም መፍጠር ነው፡፡ ለዚህ በሀገራችን መልካም የሚሆነው ምሳሌ አዕማድ (አነስተኛ ዕደ ጥበባት ማስፋፊያ ድርጅት) ነው፡፡ አዕማድ የሚለው ስም በአንድ በኩል የድርጅቱ ስም አሕጽሮት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ በግእዝና በአማርኛ ‹ምሰሦዎች› ማለት ነው፡፡ እነ FAO, WTO, FIFA, እና ሌሎቹ በዚህ መልክ የተፈጠሩ ናቸው፡፡
3. ድቅል አሕጽሮት፡- ፊደልን ከቃላት ጋር በማጣመር የሚፈጠሩ የአሕጽሮት ስሞች ናቸው፡፡ በእንግሊዝኛው Dormat – Digital format በዚህ መልኩ የተፈጠረ ሲሆን እስካሁን በአማርኛ የማውቀው ስም አላገኘሁም፡፡
እነዚህን መንገዶች እንዲያው ለማመላከት ያህል የጠቀስኳቸው አሕጽሮት እንዴው በደፈናው በዘፈቀደ የሚወጣ ሳይሆን አስበውበትና ተጠብበውበት የሚያወጡት መሆኑን ለመጠቆም ያህል ነው፡፡ ቢቻል ደግሞ ሞልቶ ከተረፈን ቋንቋ የራሳችንን ሀገር ቋንቋ አሕጽሮቶች ብንጠቀም ኩራትም ማንነትም ይሆንልናል፡፡ ባለሞያዎቹ እንዲያውም ቋንቋው ባለሆኑ ፊደሎች የተመሠረቱ አሕጽሮቶችን ‹‹Immigrant acronyms› ይሏቸዋል፡፡ የተሰደዱ አሕጽሮቶች እንደ ማለት ነው፡፡ ሰሞኑን እንዲያውም ሕገወጥ ስደት የሀገሪቱ መወያያ ጉዳይ እየሆነ ነውና እኛም ቢያንስ በሕገ ወጥ መንገድ እየተሰደዱ የሚመጡ ቃላትን ሃይ ብንላቸው ከመደናገረም፣ ከመወናገርም እንድን ይመስለኛል፡፡

አሁን ያለንበት ወቅት አብዛኞቹ ትምህርት ቤቶች ተዘግተው ልጆቻችን ቤት ውስጥ መዋል የጀመሩበት፣ ወይም የክረምት መክረሚያ ነገሮችን ማከናወን የጀመሩበት ጊዜ ነው፡፡ በበጋ ከነበረው የወላጆች ወከባ ዐረፍ ብለናል፡፡ ልጆችን ትምህርት ቤት ማድረስ፣ የቤት ሥራ ማሠራት፣ ግዙ፣ አምጡ፣ ኑ፣ ሂዱ ከሚሉ የትምህርት ቤቶች ትእዛዞች ዐረፍ ያልንበት ሰሞን ነው፡፡ አሁን ልጆቻችንን ስለሚመለከቱ ሌሎች ጉዳዮች ለመነጋገር ምቹ ጊዜ ነው፡፡ እኔ ሁለት ጉዳዮችን መርጫለሁ፤ ዛሬ አንደኛውን እናንሣው፡፡
ጉዳይ አንድ
ባለፈው ሰሞን አንዲት እናት ወደ ቢሮዬ መጥተው እንዲህ አወጉኝ፡፡ ‹‹ልጄ የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅና የ 5ኛ ክፍል ተማሪ ነው፡፡ አልፎ አልፎ የማይበት ጠባይ ግራ የሚያጋባኝ እየሆነ ተቸግሬ ነበር፡፡ ወደ ትምህርት ቤት ሲሄድ የእኔን ሽቱ ይቀባል፡፡ እኔም ይህን ሳይ የልጅ ነገር አድርጌ ትቼው ነበር፡፡ በኋላ ግን ከሌላው ነገር ጋር ሲደረብብኝ ነው ግራ የተጋባሁት፡፡ ፀጉሩን እንደ ሴቶች ማስተኛት ይፈልጋል፡፡ ጥብቅ ያለ ሱሪ ካልገዛሽልኝ ይለኛል፡፡ አንድ ቀን ትምህርት ቤት አድርሼው መኪናዬን አዙሬ ልመለስ ስል ከኋላ ያለውን መኪና እንዳልነካው ዞር አልኩ፡፡ ያን ጊዜ ያየሁትን ነገር ዓይኔ ሊያምን አልቻለም ነበር፡፡ ከአንድ ሌላ ወንድ ልጅ ጋር ከንፈር ለከንፈር ሲሳሳሙ አየኋቸው፡፡ ከኋላዬ የነበረው መኪና በጡሩንባ እየጮኸብኝ እንኳን የማየውን ተጠራጥሬ ለረዥም ሰዓት ፈዝዤ ነበር፡፡

 ሥራ ከገባሁ በኋላ እጅግ ፈዝዤ ነበር፡፡ የቢሮ ሰዎች ሁሉ እየደጋገሙ ምን እንደሆንኩ ይጠይቁኝ ነበር፡፡ ግን ለማን ምን ብዬ ልንገረው? ነገሩ እጅግ አሳፋሪ ነው የሆነብኝ፡፡ ቢቸግረኝ ወደ አንዲት ጓደኛዬ ባለቤት ጋር ደወልኩ፡፡ እርሱ ሐኪም ነበርና ምናልባት ከረዳኝ ብዬ አሰብኩ፡፡ በስልክ አነጋገሬ አደጋ የደረሰብኝ ይመስል ስለነበር እየከነፈ ቢሮዬ መጣ፡፡ ከእርሱ ጋር ተያይዘን ወጣንና አንድ ቦታ ቁጭ አልን፡፡ በልጄ ላይ ያየሁትን ነገር ሁሉ ነገርኩት፡፡ እርሱም ከሌሎች የሰማቸውን የባሱ ነገሮች እየነገረ አጽናናኝ፡፡ ከዚያም የበለጠ ርግጠኛ ለመሆንና ችግሩንም በሚገባ ለመረዳት ልጄ በማይኖርበት ሰዓት የልጄን ዕቃዎች እንድፈትሻቸው ነገረኝ፡፡

አንድ ቀን አባቱ ወደ መዝናኛ ቦታ እንዲወስደው ነገርኩትና እኔ ዕቃዎቹን መፈተሽ ጀመርኩ፡፡ ያኔ ነው የልጄን ጉዳይ በጥልቀት የተረዳሁት፡፡ እኔ ያልገዛሁለት አንድ ቀይ ቲሸርት አገኘሁ፡፡ ቲሸርቱ ላይ በእንግሊዝኛ ‹I am a gay› የሚል ተጽፎበታል፡፡ ዕንባዬን መቆጣጠር አልቻልኩም፡፡ አልጋው ላይ ተቀምጬ ለረዥም ጊዜ አለቀስኩ፡፡ ከዚያ በኋላ መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ልጄን እንዳጣሁት ገባኝ፤ ልጄን እንደማላውቀው ገባኝ፤ ልጄና እኔ በተለያዩ መንገዶች እየተጓዝን መሆኑ ገባኝ፡፡
የጓደኛዬ ባለቤት በጉዳዩ ላይ እንዴት ከልጄ ጋር ልወያይ እንደምችል መንገዶችን አመላከተኝ፡፡ አንድ ቀን ከልጄ ጋር ከአዲስ አበባ ወጣ አልን፡፡ አብሬው ስጫወት ዋልኩና ለሻሂ ዐረፍ ስንል አንድ ስልክ አነሣሁ፡፡ እንደ ደነገጠ ሰው ሆኜ ነበር የማወራው፡፡ ልጄም ድምፄን እየሰማና ሁኔታዬን እያየ ተደናገጠ፡፡ ስጨርስ ምን እንደሆንኩ ጠየቀኝ፡፡ ‹‹አንዲት ጓደኛዬ ከባድ ነገር እንደ ደረሰባት፡፡ ልጇ ግብረ ሰዶማዊ እንደሆነባት፡፡ በዚህም ምክንያት በሕግ ሊጠየቅ መሆኑን›› ነገርኩት፡፡ እጅግ ደነገጠ፡፡ ‹‹የእኔ ልጅ መቼም እንዲህ ያለ ነገር አያደርግም›› ብዬ ተውኩት፡፡ አፍጥጦ ዓይን ዓይኔን ያየኝ ነበር፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ነገር ነው የገጠማት፤ ግብረ ሰዶማዊ ማለትኮ በሃይማኖታችንም ትክክል አይደለም፤ እግዚአብሔር ግብረ ሰዶማውያንን አጥፍቷቸዋል፡፡ ከዚያም በላይ ግብረ ሰዶማውያን በኅሊናቸውም ሆነ በማኅበራዊ ኑሮአቸው ላይ ችግር እንደሚገጥማቸው፤ ከሕዝቡም እንደሚገለሉ፤ አኗኗራቸውም ከተፈጥሮ ሕግ ውጭ እንደሆነ፤ ወንድ ከሴት ጋር ሴትም ከወንድ ጋር እንጂ ወንድ ከወንድ፣ ሴትም ከሴት ጋር የሚደረገው ግንኙነት እንስሳት እንኳን የማይፈጽሙት መሆኑን፡፡ የወሲብ ግንኙነት ማንኛውም ወንድ ከ ተፈቀደለት ሴት ጋር ብቻ፣ ባህሉና እምነቱ፣ ሕጉም በሚፈቅደው እድሜና ሁኔታ የሚፈጸም መሆኑን›› እየዘረዘርኩ መግለጥ ጀመርኩ፡፡ ዝም ብሎ ነበር የሚያዳምጠኝ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ልጆቻቸውን ግብረ ሰዶማውያን እንደሚያደርጓቸው፤ እነዚህ ልጆችም ሌሎችን ልጆች አባብለው ወደዚህ እንደሚያስገቧቸው፤ እንዲያውም  ‹I am a gay› የሚል ልብስ የሚለብሱ እንዳሉ ነገርኩት፡፡
ግራ ሳይገባው አልቀረም፡፡ ስለ እርሱ እንደምናገር ገምቷል፡፡ ስጨርስ ‹‹የኔ ልጅ አንተ ግን እንደዚህ አታደርግም አይደል?›› አልኩት፡፡ ምንም አላለኝም፡፡ ዝም አለኝ፡፡ መሬት መሬት ያይ ጀመር፡፡ ‹‹ምነው የኔ ልጅ ችግር አለ እንዴ›› አልኩት፡፡ ዝም አለ፡፡ ‹‹አደራህን አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ያሉ ልጆች ሌሎች ልጆችን ሳያውቁት ወደዚህ ነገር እያስገቧቸው ነውና ተጠንቀቅ›› አልኩት፡፡ እሺም እምቢም አላለኝም፡፡ ‹‹አንተ ይህንን ስታደርግ ካየሁ፤ እኔ ወዲያው ነው የምሞተው›› ስለው ተስፈንጥሮ መጥቶ ጭኔ ላይ ተደፋ፡፡ ሲያለቅስ ይሰማኛል፡፡ ዕንባውም እግሬን ሲያሞቀው ይታወቀኛል፡፡ እኔም እያለቀስኩ ነበር፡፡
ከብዙ የዝምታ ልቅሶ በኋላ ‹‹እማዬ እኔኮ ጌይ ሆኛለሁ›› አለኝ፡፡ ቀድሜ ባውቅም ያ ሰዓት ግን መብረቅ የመታኝ ነበር የመሰለኝ፡፡ ከልጄ አንደበት ይህንን ስሰማ ኩምሽሽ ብዬ ትንሽ የሆንኩ መሰለኝ፡፡ የማደርገው ጨነቀኝ፤ ምን ልመልስለት? ምን ልበለው? ግራ ተጋባሁ፡፡ ‹‹ለምን ልጄ? ለምን?›› አልኩት፡፡ ከእኛ ራቅ ብለው የሚያዩን ሰዎች ሁኔታዬ ግራ አጋብቷቸው ሁሉም እኔን ያያሉ፡፡
‹‹እኛ ትምህርት ቤትኮ ብዙ ልጆች አሉ›› አለኝ፡፡
‹‹ምን ምን ታደርጋላችሁ?›› አልኩት
‹‹ሽቱ ተቀብተው ይመጣሉ፤ ደግሞ አንድ ዓይነት ማስቲካ ነው የምንበላው፤ ‹I am a gay› የሚል ቲሸርት እንለብሳለን›› አለኝ፡፡
‹‹ቲሸርቱን ማን ነው የሰጣችሁ?›› አልኩት
‹‹አንድ ልጅ ነው ያመጣልን፤ ለሁላችን ሰጠን፡፡ ግን ከዩኒፎርማችን ሥር እንድንለብሰው ነግሮናል››
‹‹ሌላስ?››
‹‹ደግሞ አንድ ልጅ የጌይ ፊልም በዕረፍት ጊዜ ያሳየናል››
‹‹የት ነው የሚያሳያችሁ?››
‹‹በኪሱ የሚያመጣው ሞባይል አለ፡፡ እናቴ ናት የምትጭንልኝ ብሏል››
የምሰማውን እንዴት ልመነው?
‹‹እርሱኮ [የልጁን ስም እየነገረኝ] አባቱ ትምህርት ቤት ሲሸኘው ሁልጊዜ ከንፈሩን ይስመዋል›› አለኝ፡፡ ይኼኔ ነቃሁ፡፡ አስታወስኩ፡፡ ሰውዬውንም ዐወቅኩት፡፡ እኔም ደስ አይለኝም ነበር፡፡ አባት ወንድ ልጁን፣ እናትም ሴት ልጇን ከንፈራቸውን መሳም እዚህ ትምህርት ቤት የማየው ነገር ነው፡፡ ይህ ነገር ልጆቻችን ይህንን መሰሉን ተግባር ከዕድሜ ቀድመው እንዲለምዱት ያደርጋል፡፡ ከዚያም አልፎ ነገ ሌሎች ግብረ ሰዶማውያን በልጆቹ ላይ ይህንን መሰል ተግባር ሲፈጽሙባቸው ምንም እንዳይመስላቸውና የፍቅር መግለጫ አድርገው እንዲወስዱት  ያደርጋቸዋል፡፡ ከባህላችን ያፈነገጡ ነገሮችን በልጆቻችን ላይ ማድረግ እነዚህ ነገሮች በልጆቻችን ላይ በሌሎች አካላት ሲደረጉባቸው እንዳያስተውሉት እንዳይጸየፉትም ያደርጋቸዋል፡፡
‹‹ለመሆኑ አብራችሁ ስትሆኑ ምን ታደርጋላችሁ?›› አልኩት፡፡
‹‹አንዳንድ ወንዶች ልጆች ይሳሳማሉ፤ እኔ ግን ይደብረኛል፤ ደግሞ ይተሻሻሉ›› አለኝ፡፡ ከገጽታው የመቅፈፍ ስሜት አየሁበት፡፡ ይህንን ስሜት ስመለከት ወደ ችግሩ ውስጥ ዘልቆ እንዳልገባበት ተረዳሁ፡፡ እኔ የማዝነው በባህላችን ተከብሮ የኖረውን የወንድም ለወንድም፣ የእኅት ለእኅት ግንኙነት ግብረ ሰዶማዊነት እያጠፋብን በመሆኑ ነው፡፡ እኔ ከአክስቶቼ ልጆች ጋር አብሬ እየተጫወትኩ፣ አብሬ እየተኛሁ ነው ያደግኩት፡፡ ልጆቻችን ግን እንዲህ ማድረግ ላይችሉ ነው፡፡ ከአጎታችን፣ ከአክስታችን ጋር መተኛት ለኛ ደስታችን ነበር፡፡ ዛሬ ግን ዘመዶች በዘመዶች ላይ እንዲህ የሚፈጽሙ ከሆነ ዝምድናችን ሊጠፋብን ነው፡፡ መምህሮቻችንን፣ የሃይማኖት አባቶችን፣ የቤት ሠራተኞችን፣ የጥበቃ ሠራተኞችን እየተጠራጠርን ልንኖር ነው፡፡ ግብረ ሰዶምነት ባህላችንን እጅግ አድርጎ ነው የሚያበላሸው፤ ማኅበራዊ ግንኙነቶቻችንን ነው የሚበጣጥሰው፤ እንዴት ያለ ችግር ውስጥ ነው የገባነው በእግዚአብሔር?
በኋላ ከአንዳንድ የሕክምና ባለሞያዎች ጋር ስንነጋገር  ብዙ ነገር ሰማሁ፡፡ በከተማችን ውስጥ የግብረ ሰዶማውያን ማዘውተሪያዎች የታወቁ ናቸው፡፡ የራሳቸው የመግባቢያ ‹ቋንቋም› አላቸው፡፡ ትልልቆቹ ግብረ ሰዶማውያን ድራግ በመውሰድ ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ እጅግ የሚያሳዝነው ደግሞ ለሕፃናቱ ድራጉን በከረሚላ መልክ ይሰጧቸዋል፡፡ ከወላጆቻቸው ለመደበቅ ሲሉ ልጆቹ ግለኛነትን ይመርጣሉ፡፡ ከሌሎች ልጆች ወይም ከዘመዶቻቸው ጋር ከመጨዋት ይልቅ ከጌምና ከቴሌቭዥን ጋር ብቻ መሆንን ይፈልጋሉ፡፡ በተለይም ፌስ ቡክን በሚገባ ለዚህ አስተሳሰብ ማራመጃ ይጠቀሙበታል፡፡ ወላጆች ኢንተርኔትን ልጆቻችን ያለእድሜያቸው እንዳይጠቀሙበት ማድረግ አለብን፡፡ ስለ ኢንተርኔት አጠቃቀም፣ ስለ ጥቅምና ጉዳቱ ሳንነግራቸው ነው የምንፈቅድላቸው፡፡ ይኼኔ ከበጎው ይልቅ ክፉውን የመያዝ ዕድላቸው ይሰፋል፡፡ በቤታችን ውስጥ ያስገባናቸውን የቴሌቭዥን ቻነሎችንም መቆጣጠር አለብን፡፡ ልጆቻችን ክፉውንም ደጉንም ዝም ብለው እንዲያዩ ማድረግ የለብንም፡፡ ግብረ ሰዶምን የሚያበረታቱ ቻነሎች አሉ፡፡
‹አሁን ልጅዎ ከችግሩ በሚገባ ወጥቶልዎታል?›› አልኳቸው፡፡
‹‹ሙሉ በሙሉ ከችግሩ ወጥቷል ማለት አልችልም፤ አሁንም እጠራጠራለሁ፡፡ ፍርሃቱ ገና አልለቀቀኝም፡፡ ነገር ግን ክትትሌን አላቆምኩም፤ ከልጄ ጋር ያለኝን ቀረቤታም ጨምሬያለሁ፤ ስለ ብዙ ነገሮችም እንነጋገራለን፤ የሃይማኖት ትምህርት እንዲማርም እያደረግኩ ነው፡፡ አንድ የማውቀው የሥነ ልቡና ባለሞያ ስለ ግረ ሰዶም ጉዳት በሚገባ ነግሮታል፡፡ በተለይ በዚህ ክረምት የተለየ ነገር ለማድረግ እየሞከርኩ ነው፡፡ ትምህርት ቤቶቻችንን ግን ከትምህርት ጥራትና ከክፍያቸው ባለፈ ወላጆች መከታተል አለብን፤ ልጆቻችንም የተለየ ነገር ሲያዩ እንዲነግሩን ማሳሰብ ይገባል፡፡ ዘመኑ ወላጅነት ከባድ የሆነበት ጊዜ ነው፡፡ ›› አሉኝ፡፡
ወላጆች ሆይ
እስኪ በጉዳዩ ላይ እንምከርበት፡፡ ከልጆቻችንም ጋር እንነጋገር፤ መምህራን በተማሪዎች ላይ ይህንን ነገር ፈጽመዋል ተብለው የሚከሰሱበት ጊዜ ላይ ነንና ልጆቻችን እንዳይታለሉ እንንገራቸው፤ ከሃይማኖት፣ ከሥነ ምግባር፣ ከባህል፣ ከጤናና ከማኅበራዊ ኑሮ አንጻር የሚያስከትለውን ችግር እንንገራቸው፡፡ እኛም ስለዚህ ጉዳይ መረጃ እንዲኖረን እንጠይቅ፣ እናንብብ፣ እንመካከር፤ ከተለያዩ አካባቢዎች ከምሰማው አንጻር በተለይ በከተሞች ውስጥ ችግሩ ሳይታሰብ ሥር እየሰደደ ነው፡፡ ሰሞኑን የቀረበ አንድ ይፋ ያልሆነ ጥናት በአዲስ አበባ ከተማ መሰናዶ ትምህርት ቤቶች በሚማሩ 2000 ተማዎች ላይ በተደረገ ጥናት 48% ተማሪዎች የጌይና ሌዝቢያን ደጋፊ መሆናቸው ታውቋል፡፡ እኒህ እናት እንዳሉት በዚህ ዘመን ወላጅነት ፈተና ውስጥ ገብቷል፡፡ ኃላፊነቱ ሰፍቷል፡፡ መሰናክሉ በዝቷል፡፡ እስኪ የፈጣሪን ርዳታ እየጠየቅን ይህንን ነገር የሰሞኑ የቤተሰብ አጀንዳ  እናድርገው፡፡

click here for pdf አንዳንዱ የሞተበት ቀን የድል ቀን ተብሎ ይከበርበታል፤ ሕዝብ የመሞቻውን ቀን የሚናፍቁለት ሰውም አለ፡፡ አንዳንዱ እንኳን ተወለደ ሳይባልለት…

click here for pdf ኢትዮጵያ ከቦትስዋና ጋር ስትጫወት ተገቢ ያልሆነ ተጨዋች አሰልፋችኋልና ሦስት ነጥብ ታጣላችሁ ብሎ ፊፋ የሚባል ቡዳ አገሩን ቀወጠው፡፡ እንደ

click here for pdfሐረር ከተማ የገባ ሰው ታሪካዊ ነገር የሚያምረው ከሆነ የከተማው ነዋሪ ወደ አንድ ቦታ ይወስደዋል፡፡ ቦታው ራስ ተፈሪ መኮንን የሐረር ገዥ በነበ…

click here for pdf አበሻን በአንድ እግሩ ያስቆመ፤ ለሃያ አራት ሰዓታት የመግቢያ ትኬት ፍለጋ ያሰለፈ፤ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የብሔራዊ ቡድኑን ዐርማ የያዙ ቲሸ

click here for pdf በቀደም ዕለት ከመገናኛ ወደ ሲኤም ሲ በሚወስደው መንገድ ላይ እየተጓዝን አንድ አይ ሱዙ መኪና ከጎናችን መጣ፡፡ እኛ ወደ መንገዱ ጠርዝ ተጠ

click here to read in pdf click here to read H.H. Abune Mateyas’s Speechየዘንድሮው የርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሲከፈት ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊ…

click here for pdf አንድ አባት ነበሩ፡፡ ይህ ሕዝብ እግዚአብሔርን ቢያየው ኖሮ ያምንበት ነበር፤ በእምነቱም ይጸና ነበር ብለው ያስባሉ፡፡ ስለዚህም እግዚአብ

click here for pdf ሴትዮዋ ባሏ ሞቶ ዐርባውን ታወጣለች፡፡ እንዳጋጣሚ የባሏ ዐርባና የቅዱስ ገብርኤል በዓል ይገጥማል፡፡ እርሷም ሁለቱንም እደግሳለሁ ብላ

click here for pdf ሴትዮዋ ባሏ ሞቶ ዐርባውን ታወጣለች፡፡ እንዳጋጣሚ የባሏ ዐርባና የቅዱስ ገብርኤል በዓል ይገጥማል፡፡ እርሷም ሁለቱንም እደግሳለሁ ብላ

click here for pdf በኢትዮጵያ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ ሊቅ የሆኑትና አያሌ መጻሕፍትንና የጥናት ጽሑፎችን በልዩ ልዩ ብሔራዊና ሀገር ዐቀፍ መድረኮች ያቀረቡት

click here for pdf የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ረቂቅ መመሪያ መዘጋጀቱን፣ መመሪያውም ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አንጻር የ

click here for pdf እንዴው በዚያ የደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ ሰሞን እጅግ የታወቁት የእንግሊዝ እግር ኳስ አሠልጣኝ አንዱን እንኳን የብሔራዊ ቡድናችንን …

click here for pdf እውነት እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ዘለዓለማዊ ነው፡፡ እውነትም ዘለዓለማዊት ናት፡፡ <የሰዎችን ልጆች ጥላዎች> ሲያስበረግ…

click here for pdf ሰሞኑን የፌድራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ የወጣ ረቂቅ መመሪያ› የሚል ወረቀት አስተያየት ይሰጥበት ዘንድ ለእምነ…

 click here for pdfየዛሬ ሠላሳ ዓመት በ2035 ዓም በአዲስ አበባ ትምህርት ቤቶች መካከል የአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ውድድር ይደረጋል፡፡ በውድድሩም ከዚህ በታች የማቀ

click here for pdf የዳንኤል ዕይታዎች ‹የዓመቱ በጎ ሰው› የምርጫ ኮሚቴ ሰባት አባላት ነበሩት፡፡ እነዚህ አባላት ከተለያዩ ሞያዎችና አካባቢዎች የመጡ ሲሆ

click here for pdfኃ/ገብርኤል ከአራት ኪሎ የጉባኤው ድባብሰላምና ጤናን የምመኝላችሁ፣ በሀገር ውስጥም በውጪም የምትገኙ የዚህ ጡመራ መድረክ እድምተኞች እንደም

የዚህ መ/ቤት ሠራተኞች ዘንድሮስ አምርረዋል፡፡ ባለ ስንት አሐዝ እንደፈለጉ አይታወቅም እንጂ ዕድገት ዕድገት ይላሉ፡፡ ‹ላለፉት ጥቂት ዓመታት የደረጃ ዕ

click here for pdf አንዳንዴ ትልቅ ነገር እንመኛለን፣ እንሻለን፣ እናስሳለንም፡፡ ትልቅ ሀብት፣ ትልቅ ሥልጣን፣ ትልቅ ትዳር፣ ትልቅ ቤት፣ ትልቅ ዘመድ፣ ትል

click here for pdf ‹‹አንድ ቀን ነው፤ ባለቤቴ ከበረራ የምትመለሰው ሌሊት ስለሆነ በግማሽ ልቤ ተኝቼ ስልኳን እጠብቅ ነበር፡፡ እኩለ ሌሊት ላይ ስልኬ ጮኸ፡፡ እኔ…

 click here for pdf ሰሞኑን በከተማችን በአዲስ አበባ ‹ነቢዩ ኤልያስ መጥቷል፣ የዓለምም ፍጻሜ ቀርቧል› የሚሉ አካላት ተነሥተዋል፡፡ እነርሱ እንደሚሉትም ነ

በአቡነ አትናቴዎስ መቃብር ላይ የበቀለው ዋርካ በሩቅ ሲታይclick here for pdf ደብረ ጽሞና ገዳም ውስጥ በአንዲት ጠባብ ጎጆ ለሦስታችንም መደብና ምድር ላይ ተ

click here for pdf የ‹ዳንኤል ዕይታዎችን› ሦስተኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ ኢትዮጵያውያን በጎ አሳቢዎችና ሠሪዎች ዕውቅና ያገኛሉ፡፡ ለዚህ ምርጫ ‹በጎ

click here for pdf  የዳንኤል ዕይታዎች የጡመራ መድረክ ሦስተኛ ዓመት ሚያዝያ 5 ቀን ከቀኑ ሰባት ሰዓት ጀምሮ በአዲስ አበባ ይከበራል፡፡ በዚህ ዝግጅት ላይየተ…

click here for pdfከሀገር ወጣ ብዬ የተለያዩ ሀገሮች ስዘዋወር ከምቀናባቸው ነገሮች አንዱ የደንበኞች አያያዛቸው ነው፡፡ ‹ደንበኛ ንጉሥ ነው› የሚለው እዚያ በገ