የሃይማኖት ተቋማት ምዝገባ መመሪያ፣ አንዳንድ ነጥቦች


የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ረቂቅ መመሪያ መዘጋጀቱን፣ መመሪያውም ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አንጻር የማያስኬድባቸውን አጠቃላይ ጉዳዮች ባለፈው አንሥተን ነበር፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን ሲገመግም በሕግ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኩል ካነሣቸው ነጥቦች አንዱ ወደ ምክር ቤቱ የሚመጡ ሕጎች በሚገባ ረቅቀው፣ ተሰልቀውና የማያዳግሙ ሆነው ከመምጣት ይልቅ በሚገባ ሳይዘጋጁ በመምጣታቸው በጥቂት ጊዜ ውስጥ ማሻሻያ በማውጣት የምክር ቤቱ ጊዜ እየባከነ፣ የሕጎችንም ደረጃ እያስገመተ መሆኑን ነው፡፡ አሁንም ይህ የሃይማኖት ተቋማትን ለመመዝገብ የወጣው መመሪያ ምክር ቤቱ የሰጠውን ተግሣጽ የተከተለ ይሆን ዘንድ ሊታዩ የሚገባቸውን ሃሳቦች አቅርበናል፡፡

 የዐዋጁን በጆሮ

 የፍትሐ ብሔር ሕጋችን በዐንቀጽ 398 ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ ሰውነት ይሰጣታል፡፡ ሌሎች የሃይማኖት ተቋማትን የተመለከተ ልዩ ሕግ እንደሚወጣ፤ ልዩ ሕጉ ካልወጣም ስለ ማኅበራት በተደነገጉ ድንጋጌዎች እንደሚተዳደሩ ዐንቀጽ 407 ይገልጣል፡፡ ይህ ድንጋጌ የወጣው በዐዋጅ ደረጃ ነው፡፡ መሻሻልም ካለበትም በዐዋጅ ነው፡፡ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ግን የዐዋጁን በጆሮ ሊያሻሽለው ነው የተነሣው፡፡ መመሪያ በሕግ ተዋረድ ውስጥ የመጨረሻው ደረጃ ነው፡፡ ዐዋጅና ደንብ በነጋሪት ጋዜጣ እንዲወጡና ማኅበረሰቡም እንዲያውቃቸው የሚያደርግ ሕግና አሠራር ሲኖር መመሪያ ግን በአንድ መሥሪያ ቤት የሚወጣና የመታወቅ ዕድሉም ሕዝባዊ ያልሆነ ነው፡፡ ሃይማኖትን የሚያህል ጉዳይ በመመሪያ ለመወሰን መነሣት የዐዋጁን በጆሮ እንደማድረግ ነው፡፡
ፖሊሲው የት አለ?
ኢትዮጵያን በሚያህል 97% የሚሆነው ሕዝቧ ሃይማኖተኛ በሆነባት ሀገር እስከ ዛሬ ድረስ የሃይማኖት ፖሊሲ የላትም፡፡ ሃይማኖት የሕዝቡን የዕለት ተዕለት ሕይወት፣ ርዕዮተ ዓለምና ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማኅበራዊ ጉዳዮች ለመወሰን ዋነኛው ግብዐት በሆነባት ኢትዮጵያ ፖሊሲ ሳይኖር በአንድ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ደረጃ የሃይማኖት ጉዳዮችን መመልከት፣ ብሎም ሃይማኖትን የተመለከተ መመሪያ ማውጣት ስሕተት ነው፡፡ የፖሊሲ ሃሳብ ቢመነጭና በፖሊሲ ላይ ውይይት ቢደረግ ኖሮ ሃይማኖት በሀገሪቱ ጉዞ ላይ ያለውን ተጽዕኖ፣ የሃገሪቱን ጉዞ በመወሰን ረገድ ሃይማኖት ሊኖረው የሚገባውን ቦታ፣ በእምነቶች መካከል ሊኖር ስለሚገባው ግንኙነት፤ የሃይማኖት ጎዳዮች አወሳሰን መርሖች፣ የሃይማኖት ጉዳዮችን ለመወሰን የሚያስፈልገውስ መመሪያ ነው? ዐዋጅ ነው? ወይስ ደንብ? የሚለውን ለመወሰን፤ የሃይማኖት ተቋማትም በሀገሪቱ የልማት፣ የዴሞክራሲ፣ የሰብአዊ መብት ጥበቃ፣ የሥነ ምግባር እነፃ ሊኖራቸው የሚችለውን ሱታፌ ለማስፈር የፖሊሲው መኖር ወሳኝ ነው፡፡
ለሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች በዐዋጅ ከተሰጡ ሥልጣኖች አንዱ ይህንን መሰል ፖሊሲዎችን ማመንጨት ነው፡፡ በሀገራችን ከሃይማኖት ባነሰ ሁኔታ ማኅበረሰባችንን ለሚገዙ ነገሮች ፖሊሲ ተቀርጾላቸዋል፡፡ የሃይማኖት ጉዳዮችን የሚመለከት ሀገራዊ ፖሊሲ ግን የለንም፡፡ ስለዚህም የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ሥራውን ከፖሊሲ ይጀምር፡፡
አሳንሶ ማየት
በኢትዮጵያ ውስጥ ማኅበራትና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ያላቸው ሚና ታላቅ ቢሆንም የሃይማኖትን ያህል ግን ለኅብረተሰቡ ቅርብ፣ የኅብረተሰቡን ኑሮ ወሳኝና በኅብረተሰቡም ላይ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች አይደሉም፡፡ 97% ኢትዮጵያዊ በሀገሪቱ የሚገኙት እምነቶች ተከታይ ነኝ ብሏል፡፡ ማኅበራትና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ግን የዚህን አንድ ሃያኛ ሕዝብ እንኳን የማሰለፍና የማሳመን፣ በተጽዕኖ ክልላቸውም ሥር የማስገባት ዐቅም የላቸውም፡፡ ሀገሪቱ የማኅበራትንና የበጎ አድራጎት ድጅቶችን ጉዳይ በዐዋጅ ስትደነግግ የሃይማኖትን ጉዳይ ግን በአንድ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤት መመሪያ መደንገጓ ለእምነት ተቋማት ካለው ግምት ይልቅ ለማኅበራትና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች የሚሰጠው ግምት የሚበልጥ መሆኑን ያሳያል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ኢትዮጵያ ውስጥ የሃይማኖት ጉዳዮች ሚኒስቴር ያስፈልግ ነበር፡፡ የኢትዮጵያን የእምነት ጉዳዮች በተመለከተ ፖሊሲ የሚያረቅቅ፣ ሃሳብ የሚያመነጭ፣ ከሀገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር የሚያዛምድ፣ በመንግሥት ጉዳዮች ውስጥም የሃይማኖት ነገሮች ተገቢውን ትኩረት እንዲያገኙ የሚያደርግ ራሱን የቻለ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያስፈልግ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሃይማኖት ተጽዕኖ ከባህል በላይ ነው፡፡ባሕል በሚኒስቴር ደረጃ ሲታይ ሃይማኖትን በመምሪያ ወይም በዳይሬክቶሬት ደረጃ ማስቀመጥ በሬውን በድስት ዶሮን በሰታቴ ነው የሆነው፡፡
ከሕገ መንግሥቱ ጋር ይቃረናል
የሃይማኖትና የእምነት ነጻነት የሰዎች ልጆች መሠረታዊ መብቶች ከሚባሉት ነጻነቶች መካከል ናቸው፡፡ ማንኛውም ሰው ከሚመስሉት ጋር በጋራም ሆነ በግሉ የፈለገውን ነገር ለማምለክ ይችላል፡፡ ይህንን መብት ማገድ የሚቻለው ‹የሕዝብን ደኅንነት፣ ሰላም፣ ጤና፣ ትምህርት፣ የሞራል ሁኔታዎችን፣ የሌሎች ዜጎችን መብቶች፣ ነጻነቶችና መንግሥት ከሃይማኖት ነጻ መሆኑን ለማረጋገጥ በሚወጡ ሕጎች ብቻ›› መሆኑን ሕገ መንግሥቱ ይደነግጋል (ዐንቀጽ 27፣ 5)፡፡
አዲስ በተረቀቀው የሃይማኖት ተቋማት ምዝገባ መመሪያ ላይ ግን የሃይማኖት ተቋማት አስፈላጊውን መመዘኛ አላሟሉም ብሎ ካመነ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ምዝገባ የሚከለክልበት መብት ተሰጥቶታል(ቁ5፣6፣7፣8፣9)፡፡ይህ ከሆነ ደግሞ ሦስት ነገሮችን ያስሣል፡
  1. በሕገ መንግሥቱ የእምነትና የሃይማኖት ነጻነት ገደብ ይጣልበታል ብሎ ካስቀመጠው ሃሳብ ጋር ይጋጫል፡፡ በዚህ የሕገ መንግሥቱ ዐንቀጽ ውስጥ ‹መመዘኛ ካላሟሉ› የሚል ሃሳብ ፈጽሞ የለምና፡፡
  2. እነዚህን መብቶች ለመገደብ የሚወጣው ሕግ ‹የሕዝብን ደኅንነት፣ ሰላም፣ ጤና፣ ትምህርት፣ የሞራል ሁኔታዎችን፣ የሌሎች ዜጎችን መብቶች፣ ነጻነቶችና መንግሥት ከሃይማኖት ነጻ መሆኑን ለማረጋገጥ በሚወጡ ሕጎች ብቻ›› መሆኑን ሕገ መንግሥቱ ይደነግጋል፡፡ ይህ አሁን የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ያወጣው ሕግ የትኞቹን ለመተግበር የወጣ ሕግ ነው?
  3. የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ አንድን የእምነት ተቋም አልመዘግብህም ካለው ያ የእምነት ተቋም ሕጋዊ አይሆንም፡፡ በውስጡ የሚከናወኑ ጉዳዮችም ሁሉ ሕገ ወጥ ተግባራት ይሆናሉ ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤትንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ያላሟላችሁት ነገር አለና አልመዘግብም ቢል ቅዳሴ መቀደስ፣ ማኅሌት መቆም፣ ክርስትና ማስነሣት፣ አዛን ማሰማት፣ ሶላት መስገድ፣ ዱአ ማድረግ ሕገወጥ እንቅስቃሴ ሊሆን ነው ማለት ነው? ይህ ከሆነ ደግሞ ሕገ መንግሥቱ የሰጠው መብት በመመሪያ ተጣሰ ማለት ነው፡፡
የመንግሥትን ለእምነት ተቋማት
በረቂቅ መመሪያው ዐንቀጽ 18/5 ላይ የሃይማኖት ተቋማት በሃይማኖት ሽፋን የሚደረጉ ጸረ ሰላም፣ አክራሪነትንና ጽንፈኛነትን እንቅስቃሴዎች የመከላከል ግዴታ አለባቸው ብሏል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ እነዚህ ነገሮች በሀገሪቱ ሕጎች በግልጽ ‹ወንጀል› ከተባሉ ወንጀልን መከላከል የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት ነው፡፡ ተቋማዊ በሆነ መንገድ መከላከል ደግሞ የመንግሥት ኃላፊነት ነው፡፡ ምክንያቱም በግልጽ ‹ወንጀል› ብሎ በሀገሪቱ ሕጎች የተደነገገውን የፈጸመን አካል የመክሰስ፣ ከስሶም የማስቀጣት ተቋማዊም ሕጋዊም ኃላፊነት ያለበት መንግሥት ነውና፡፡ በሁለተኛ ደረጃም እነዚህ የእምነት ተቋማት የማስተማርና በእምነታቸው መሠረት የማይሄደውን የማውገዝ እንጂ ከዚህ ያለፈ ተግባር ማከናወን አይችሉም፡፡ በመሆኑም በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱና በእምነት ተቋማቱ መካከል ‹አልተከ ላከላችሁም› ‹ተከላክለናል› የሚለውን ክርክር የመዳኛ መሥፈርት ማግኘት ከባድ ነው፡፡
አንድን የእምነት አካሄድስ ‹አክራሪና ጽንፈኛ› ብሎ የሚተረጉመው ማነው? መጀመሪያስ በእነዚህ ጽንሰ ሃሳቦች ላይ ስምምነት ተደርሷል ወይ? ይህ ሁሉ ኃላፊነት የመንግሥት እንጂ የእምነት ተቋማት ሊሆን አይችልም፡፡ ለሃይማኖት ተቋማት ይህን አስተምሩ፣ ይህንን ተከላከሉ፣ ይህንን አውግዙ፣ ይህንን ተቆጣጠሩ የሚል መመሪያ ከመንግሥት ይሰጥ ዘንድ ሕገ መንግሥቱ አይፈቅድም፡፡ የእምነት ተቋማት አስተምህሯቸውን የሚወስኑት ራሳቸው ናቸው፡፡ ሌላ አካል ሊሆን አይችልም፡፡ ይህንና ያንን ስላላስተማራችሁ፣ ስላልተከላከላችሁ ትኖሩ ዘንድ አልፈቅድላችሁም ማለትም አይቻልም፡፡
ከሌሎች ጋር የሚኖር ግንኙነት
በረቂቅ መመሪያው ላይ (19/5) የሃይማኖት ተቋማት በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ከሚገኙ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመቃረን ከሚንቀሳቀሱ አካላት ጋር ማንኛውንም ዓይነት ግንኙነት መፈጸም እንደሌለባቸው ይገልጣል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ይህ ድንጋጌ ለእምነት ተቋማት ለምን አስፈለገ? በሀገሪቱ ሕጎች ውስጥ ማንኛውም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝ ተቋም ከእነዚህ አካላት ጋር መገናኘት እንደሌለበት ከተደነገገ በቂ ነው፡፡ በሌላም በኩል ‹ግንኙነት› የሚለው ቃል ዝርዝር የሆነና ሁሉን የሚያስማማ ትርጉም የሚሻ ነው፡፡ አንድ የንስሐ አባት በአንድ በሕግ የተከለከለ ድርጅት ውስጥ ለሚገኝ ሰው ንስሐ መስጠት አይችሉም ማለት ነው? ከላይ በተደነገገው ድንጋጌ ውስጥ በሚካተት ድርጅት ያለ ሰው ወደ አንድ አጥቢያ መጥቶ ማስቀደስ አይችልም ማለት ነው? ፍትሐትና ተዝካር አይደረግለትም፣ ልጆቹ ክርስትና አይነሡለትም ማለት ነው? ይህ ከሆነ ደግሞ እንድ ሰው የእንድ እምነት ተከታይ ሆኖ አገልግሎት ለማግኘት ከመሠረታዊ የሃይማኖት ድንጋጌ በተጨማሪ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱን መመሪያም መቀበልና መተግበር ሊጠበቅበት ነው ማለት ነው፡፡ ወይም የአንድ እምነት ተከታይ ለመሆን ፖለቲካዊ አዝማሚያ መታየት ሊኖርበት ነው ማለት ነው፡፡
የእምነት ተቋማቱ እንደ ተቋም ‹በሕግ የተከለከለ› ተቋም ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንዳያደርጉ መደንገጉ ተገቢ ሊሆን ይችል ይሆናል፡፡ እርሱም ቢሆን ‹ሕገ መንግሥታዊውን ሥርዓት ተቃርኗል› ብሎ የሚወስነው ማነው? የሚለው ወሳኝ ነው፡፡ መንግሥት በሕግ በዚህ ዘርፍ የሚመድባቸው ተቋማት አሉ፡፡ ከእነዚህ ዓይነት ተቋማት ጋር መደረግ ስለሌለባቸው ግንኙነቶችም መወሰን ያለበት በዝርዝርና በሕግ እንጂ በአንድ መሥመር መሆን የለበትም፡፡
በአጠቃላይ ረቂቅ መመሪያው በአንድ መሥሪያ ቤት ወጥቶ፣ ዳኝነቱንም ለዚያው መሥሪያ ቤት መልሶ የሚሰጥ(ቁ 32፣32/1/መ) ሃይማኖትን የሚያህል ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኝን ነገር አንድ ሚኒስትር እንዲወስንበት የሚያደርግ፣ በኢትዮጵያ የሚገኙ የተለያዩ የእምነት ተቋማትን ጠባይ ከግምት ውስጥ ያላስገባ (በተለይም ኦርቶዶክስን፣ ካቶሊክንና እስልምናን)፣ በመሆኑ ተጣድፎ በማጽደቅ በሀገሪቱ ላይ እምነት ለኮስ ጭቅጭቅና መሻከር ከመፍጠር ይልቅ አስቀድሞ የሀገሪቱን የእምነት ፖሊሲ ማርቀቅ፣ በረቂቁም ላይ ጊዜ ወስዶና ሁሉንም አሳትፎ ውይይት ማድረግ፣ የልዩ ልዩ ሊቃውንትንና ምሁራንን ሃሳብ ማድመጥ፣ ከዚያም በፖሊሲው ላይ ስምምነት በተደረሰባቸው ጉዳዮች መሠረት ቀሪውን ማከናወን የተሻለ ይሆናል፡፡