የ500 ዓመቱ ዛፍ (ክፍል ሁለት)
ደብረ ጽሞና ገዳም ውስጥ በአንዲት ጠባብ ጎጆ ለሦስታችንም መደብና ምድር ላይ ተነጥፎልን አደርን፡፡ ቤታችን ውስጥ ካለው አልጋ ይልቅ እንዴት ይመቻል መሰላችሁ፡፡ በአካባቢው ከአራዊት ድምጽ በቀር ሌላ ድምጽ የለም፡፡ ሬዲዮ፣ ቴሌቭዥን፣ ሞባይል እንዲህ ልሳናችሁ ሲዘጋ ለካስ ሰላም ይገኛል፡፡ አንዳንዴ እነዚህ የቴክኖሎጂ ውጤቶች መጠቀሚያዎቻችን መሆናቸው ቀርቶ በእኛ ላይ ሠልጥነውብን ኖሯል፡፡ አንዳንዴ ለሞባይል፣ ለኢንተርኔትና ለሚዲያ ያለን ፍቅር፣ ከፍቅርም አልፎ ያለ እነርሱ ሕይወታችን ሲጎድል፣ ከዚህ በፊት ያለ እነርሱ ኖረን የማናውቅ ነው የምንመስለው፡፡
የተነሣነው ከሌሊቱ አሥር ሰዓት ነው፡፡ አብረውን ወደ በረሃው ለመውረድ የገዳሙ ሦስት ልጆች ተዘጋጅተዋል፡፡ ጨለማው ድቅድቅ እንዳይል ጨረቃዋ ብቅ እያለች ፈገግታ ትልክበታለች፡፡ ሻምበል የያዛት ባትሪ ብርሃኗ የትራፊክ መብራት ያህል ነው፡፡ የት እንዳለን ማሳያ ትሆን ይሆናል እንጂ መንገዱን አታሳየንም፡፡ አንደኛው ልጅ ከፊት ሁለቱ ከኋላ ሆነው ወደ ሙገር በረሃ መውረድ ጀመርን፡፡
የሙገር አካባቢ በጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ታዋቂ ከሆኑት ቦታዎች አንዱ ነው፡፡ ሙገር በሦስት ነገሮች ይታወቃል፡፡ የመጀመርያው የእደ ጥበብ ባለሞያዎች የነበሩት የጋፋት ሕዝቦች ይኖሩባቸው ከነበሩት ቦታዎች አንዱ መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ አካባቢው በአምልኮ ጣዖት የበረታ አካባቢ የነበረ መሆኑ ነው፡፡ ይህንን አምልኮ ጣዖት ለማስወገድ ብዙ አባቶች በአካባቢው አስተምረዋል፡፡ በተለይም በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመን እጨጌ መርሐ ክርስቶስ በአካባቢው አምልኮ ጣዖትን ለማስወገድ ብርቱ ጥረት አድርገው ነበር፡፡ ሦስተኛው ደግሞ ሙገር በአካባቢው በነበሩ ገዳማትና ቅዱሳን የታወቀ ነው፡፡ እንደነ አቡነ አኖሬዎስና እንደነ አቡነ ተክለ ሐዋርያት የመሰሉ ቅዱሳን ከሙገር ተገኝተዋል፡፡ ከዚህም በላይ ደብረ ጽሞና፣ ደብረ ጽላሎና ደብረ ደርባ የተባሉ ገዳማት በሙገር በረሃ ውስጥ ነበሩ፡፡
|
ታሪካዊው የሙገር ቆላ
|
ሙገር በነገሥታቱ ተመራጭ ከነበሩት ቦታዎች መካከል አንዱ እንደነበር የዐፄ ሠርፀ ድንግል ዜና መዋዕል ይነግረናል፡፡ በግራኝ መሐመድ ጦርነት ጊዜም ታላላቅ ጦርነቶች ከተደረጉባቸው ቦታዎች አንዱ ሙገር ነበር፡፡ የንጉሡ ወታደሮችም በሙገር ይከርሙ ነበር፡፡
|
ሦስቱ መንገድ መሪዎቻችን
|
አሁን ጨረቃዋ ተሰናብታን ወደ ቤቷ ገባችና ዓይንን ቢወጉ የማይታይበት ጨለማ ላይ ደረስን፡፡ የሕፃን ልጅ ጭንቅላት የሚያክለው የመንገዱ ድንጋይ እግራችንን እያንዳለጠ መሬት ላይ ያነጥፈናል፡፡ ለነገሩ ባንሸራተተን ቁጥር ወደ ታች ስለምንወርድ እንደ ትብብር ነው የቆጠርንለት፡፡ ሰውዬው በሬውን ጅብ በልቶበት ጅቡን እገላለሁ ብሎ ወጣ፡፡ መንገድ ላይ አገኘውና በጦር አፉን ወጋው፡፡ ጅቡም አመለጠ፡፡ ቤቱ ሲመለስ ለሚስቱ ‹ያንን ጅብኮ አገኘሁት› አላት፡፡ ‹ታድያ ገደልከው› አለችው፡፡ ‹አይ አልጨረስኩትም፤ ግን የአፉ ጎን ላይ ወጋሁት› አላት፡፡ ‹አይ ይህማ ምኑን ጎዳኸው፣ እንዲያውም አፉን አሰፋህለት› አለችው አሉ፡፡
|
ጨረቃዋ ተሰናብታን ስትገባ
|
ገደሉን ጨርሰን ረባዳው ላይ ስንደርስ መንጋት ጀመረ፡፡ አሁን የሙገር በረሃ ወለል ብሎ ታየን፡፡ እጅግ ለምለም የሆነ ቆላ፡፡ በወንዞች የተከበበ ቆላ፡፡ በውስጡ ጅማ፣ ሸምጤና ሙገር ወንዞች የሚገማሸሩበት ቆላ፡፡ ጥንታውያን ዛፎች አሁንም ያልተለዩት፣ እዚህም እዚያም እንደ ዔላም የዘንባባ ዛፎች ቁመታቸውን ከጠፈር ጥግ አድርሰው ኒፍሌም የሚመስሉበት ቆላ፡፡ አረንጓዴው ሣር ወደ ቢጫነት መቀየር ከጀመረው ሣር ጋር ተጎዳኝቶ ስጋጃ ያለበሰው ቆላ፡፡
ከፊት ለፊታችን ደብረ ገብርማ ይታያል፡፡ የገጠር ቤተ ክርስቲያን የምታክል አረንጓዴ ቤተ ክርስቲያን ትታየናለች፡፡ ታላቁ ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሐዋርያት ለአሥራ ሦስት ዓመታት በተጉለት አባ በርሶማ ቤተ ክርስቲያን ተቀብረው ከቆዩ በኋላ ዐጽማቸው ፈልሶ የተቀበረባት ቦታ ናት ‹ደብረ ገብርማ›፡፡ ዐጽሙን በንጉሥ በዕደ ማርያም ዘመን ወደዚህ ያመጡት ደቀ መዝሙሮቻቸው ናቸው፡፡ ዐጽሙ ፈልሶ በመጣ ጊዜ የተደረጉትን ተአምራት ገድላቸው ይተርክልናል፡፡ ቦታው አሁንም ስሙን አልለቀቀም፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በቦታው ላይ ቤተ ክርስቲያን አልነበረም፡፡ አሁን ያለው ቤተ ክርስቲያን የታነጸው በ1980ዎቹ አጋማሽ ላይ ነው፡፡
|
ደብረ ገብርማ- የአቡነ ተክለ ሐዋርያት ዐጽም ያረፈበት
|
ደብረ ገብርማ ስንደርስ 12 ሰዓት ተኩል ሆኗል፡፡ ውሾቹ ግብር ለመክፈል ያህል ይጮኻሉ፤ ወፎቹ ልዩ በሆነ ኅብረ ዜማ ንጋቱን ለማብሠር ያዜማሉ፤ ዶሮዎቹም ከሠፈር ሠፈር እየተጠራሩ እንደ ብርቱ ዲያቆን ‹ተነሡ› ይላሉ፡፡ ገበሬዎቹ ደግሞ ጋቢያቸውን ተከናንበው ከብቶቻቸውን ከበረታቸው ወጣ ወጣ ያደርጋሉ፡፡
ደብረ ገብርማ ግቢው ጸጥ ብሏል፡፡ አብረውን ከሄዱት ልጆች መካከል አንደኛው ወደ መንደር ገባና ቁልፍ ያዡን ዲያቆን ጠራው፡፡ የቤተ ክርስቲያኑ በር ተከፈተ፡፡ ውስጡ እጅግ በጣም ጠባብ ነው፡፡ ይህንንም ቢሆን የሚያገለግለው አጥቶ አሁን ቅዳሴና ኪዳን ከታጎለበት ሰንብቷል አሉኝ፡፡ ከቤተ ክርስቲያኑ ጀርባ ሁለት መነኮሳት ይኖራሉ፡፡
|
እነሆ ነጋ
|
ከብትና ዶሮ በማርባት፣ የጓሮ አትክልትም በመትከል ገዳሙን የሚያገለግሉ አንዲት ብቸኛ መነኩሲት አሉ፡፡ ብርታታቸው ለጉድ ነው፡፡ አካባቢውን ከሚጠብቁት ውሾቻቸው ጋር ሆነው፤ ሥራና ጸሎትን አስተባብረው ገዳሙን ያገለግላሉ፡፡ ብቻቸውን መሆኑ እንዲያውም ተመችቷቸዋል፡፡፡ ‹ከመነኑ ወዲያ ሰው ምን ያደርጋል፤ ደግሞስ ሰው ከበዛ አገልግሎት የት ይገኛል› ብለውኛል፡፡ ‹ሰው መሆን ሰው በሌለበት ቦታ ነው› የሚል መርሕ አላቸው፡፡
እዚያው ግቢ ውስጥ እድሜያቸው ከሰማንያ የዘለሉ አንድ አረጋዊ አባት አሉ፡፡ አባ ግርማ ይባላሉ፡፡ ተወልደው ያደጉት እዚያው ገብርማ አካባቢ ነው፡፡ የቦታውን ታሪክ የነገሩንም እርሳቸው ናቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሐዋርያት የተቀበሩት በዚሁ በደብረ ገብርማ ግቢ ውስጥ መሆኑን እንጂ ትክክለኛ ቦታው ገና አልታወቀም፡፡ በግራኝ ጊዜ ገዳሙ ሲጠፋ ቤተ ክርስቲያኑም ተቃጠለ፡፡ ጽሕፈት ያለበት የድንጋይ ምልክት ለብዙ ዘመን በመቃብራቸው ላይ ነበር፡፡ በ1906/7 አካባቢ ንግሥት ዘውዲቱ ወደ ቦታው መጥተው ደብረ ጽሞናን በጥንቱ ቦታ ላይ ሊተክሉት ሲሉ የአካባቢው ባለ መሬት ገዳሙ መሬቴን ይወስድብኛል ብሎ ተቃወመ፡፡ የቦታው ምልክት እንዲጠፋም የተተከለውን ድንጋይ አስነቅሎ ገደል ከተተው ይባላል፡፡
|
አባ ግርማ አልጋቸው ላይ ሆነው ታሪኩን ሲተርኩልን
|
በብዙ ክርክርም ገዳሙ የገደሉ ወገብ ላይ ከጥንቱ ቦታ ርቆ ተተከለ፡፡ ደብረ ገብርማም ጠፍ ሆኖ ለብዙ ዘመን ኖረ፡፡ ድንጋዩ መነቀሉን ከወላጆቻቸው የሰሙ፣ ሲነቀልም በአካል ልጅ ሆነው ያዩ ሰዎች በአካባቢው አሁንም አሉ፡፡ ነገር ግን የት እንደተጣለና የትስ ተተክሎ እንደነበረ ሊያስታውሱ አልቻሉም፡፡ በአካባቢው ያገኘኋቸው ሽማግሌዎች ሁሉ በሁለት ነገሮች ላይ ይስማማሉ፡፡ መቃብሩ በገብርማ ግቢ እንደነበረና፣ በመቃብሩ ላይ ጽሕፈት የነበረበት የድንጋይ ምልክት እንደነበረ፡፡ ይህንን የድንጋይ ምልክት ብናገኘው ኖሮ በላዩ ላይ ከተጻፈው ጽሕፈትም ይሁን ምልክት ስለ ጥንታዊ ታሪካችን የምናገኘው አንዳች ነገር ይኖረን ነበር፡፡ የአርኬዎሎጂና የታሪክ ተመራማሪዎች በነገሩ ቢገፉበት እጅግ ብዙ ነገሮችን በአካባቢው ያገኛሉ፡፡
አንድ ሽማግሌ እንደነገሩን እርሳቸው ልጅ ሆነው ከብት ሲጠብቁ ልጆች ከገብርማ ግቢ አንድ ገደል ውስጥ የከበረ ዕቃ አገኙ፡፡ ወስደውም ለአባታቸው ሰጡ፡፡ አባትዬውም ወርቅ ነው ብለው ወደ አንጥረኛ ጋ ወሰዱት፡፡ አንጣሪው ግን ወርቅ አይደለም ብሎ በ30 ጠገራ ሸኛቸው፡፡ እዚህ ግቢ ውስጥ ተገቢ የሆነ የጥናት ቁፋሮ ቢደረግ ስለ ሙገር አካባቢ ክርስትና ያላወቅነውን ነገር እናገኝ ይሆናል፡፡
|
ደብረ ገብርማን የከበበው የጥንቱ እድሞ
|
ይህንን የድንጋይ ምልክት ያጠፉትን ሰው በተመለከተ በአካባቢው እንዲህ ይተረካል፡፡ የደብረ ጽሞናው (የመጀመርያው) አበ ምኔት አባ ተክለ ሃይማኖት የድንጋዩን ተነቅሎ መጣል ሲሰሙ ‹የተክለ ሐዋርያትን መቃብር እንደ ደበቅከው ያንተም መቃብር ሳይታወቅ ይቅር› ብለው ሰውዬውን ረገሟቸው፤ እኒያ ሰው ንጉሡን ተከትለው ማይጨው ዘምተው ነበር፡፡ የት እንደ ሞቱና የት እንደተቀበሩ እስከ ዛሬ አልታወቀም፡፡
ደብረ ገብርማን ለቅቀን ወጣን፡፡ አሁን ወደ ሸምጤ ወንዝ አቅጣጫ ከደብረ ጽሞና በስተ ቀኝ ልንጓዝ ነው፡፡ ወደ ደብረ ጎል፡፡ ደብረ ጎል በገድለ አቡነ ተክለ ሐዋርያት እንደተተረከው አቡነ አትናቴዎስ የተባሉ(ምናልባት በላሊበላ ዘመን የነበሩ) ደግ ጳጳስ የተቀበሩበት ቦታ ነው፡፡ ቦታውን ለአቡነ ተክለ ሐዋርያት ያሳየቻቸው እግዚእ ክብራ የምትባል በአካባቢው የነበረች እናት ናት፡፡ አቡነ ተክለ ሐዋርያት ወደ ቦታው መጥተው በቦታው ሱባኤ ይዘውበት ነበር፡፡
|
ሸምጤ ወንዝ
|
የሸምጤን ወንዝ ተሻገርንና ወደ ደብረ ጎል አቀናን፡፡ አሁን ቦታው ‹ጎለሌ› ይባላል፡፡ በአቡነ አትናቴዎስ መቃብር አካባቢ ሁለት ነገሮች ይገኛሉ፡፡ አንደኛው ከዛሬ አምስት መቶ ዓመት በፊት በመቃብራቸው ላይ የበቀለ ትልቅ ዋርካ ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ ከዋርካው አጠገብ የፈለቀው ጠበል ነው፡፡
የደብረ ጎል ዋርካ እጅግ የተለየ ዋርካ ነው፡፡ ስፋቱ ወደ አሥር ሜትር ይደርሳል፡፡ ቅርንጫፎቹ በሁሉም መዓዝናት ተዘርግተዋል፡፡ እያንዳንዱ ቅርንጫፍ ወደ ጎን ይረዝምና ምድር ተሳልሞ እንደገና ይነሣል፡፡ የቅርንጫፎቹ ርዝመታቸው ወደ ጎን ሃምሳ ሜትር ይደርሳል፡፡ ዋርካው ግዛቱን እያሰፋ አካባቢውን በክልሉ ሥር አድርጎታል፡፡ መልኩ ወደ ቢጫ የሚጠጋ ሲሆን ለቦታው ግርማ ሞገስ ሰጥቶታል፡፡ ይህ ዋርካ በረከት አለው ብለው ምእመናኑ ሽርፍራፊውን ይወስዳሉ፡፡ እኛም ለራሳችን ወሰድን፡፡
|
የ500 ዓመቱ ዋርካ
|
ከዋርካው አለፍ ብሎ ከምድር ሥር እንደ ኤርታሌ እየተንፎለፎለ የሚፈልቅ ጠበል አለ፡፡ ጠበሉ ኩልል ብሎ በቦይ ወደ ዋርካው ሥር ይሄዳል፡፡ አካባቢውንም ያረሰርሰዋል፡፡ በገድለ አቡነ ተክለ ሐዋርያት ላይ ይህ ጠበል እንዴት እንደፈለቀ ይተርካል፡፡ እንግዲህ ጠበሉም ከ500 ዓመት በላይ እድሜ አስቆጥሯል ማለት ነው፡፡
አሁን ፀሐይ ባለ በሌለ ኃይሏ ሙገርን ማስከንዳት ጀምራለች፡፡ እኛም ቀትሩ ሳይበረታ ወደ ላይ መውጣት አለብን፡፡ ‹ዝንጀሮ አይወጣውም› የተባለለት የአምባሰል ገደል ይህንን ገደል የሚስተካከለው አይመስለኝም፡፡ እኔና ሻምበል አምስት ደቂቃ እንሄዳለን፣ አሥር ደቂቃ እናርፋለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ እግሬን እኔ አላዝዘውም ነበር፤ መንገድ እንደለመደች አህያ በራሱ ጊዜ ነበር የሚራመደው፡፡ ለሦስቱ የገዳሙ ልጆች ጉዟችን ቀልድ ሆኖባቸዋል፡፡ ‹አይ ከተምቾ› ሳይሉን አልቀሩም፡፡ እነርሱ ዳገቱን ሲወጡት እንደ ጦጣ ነው፡፡
|
ከዋርካው ጎን የፈለቀው ጠበል
|
ከፊታችን የሦስት ሰዓት ዳገት ነው የሚጠብቀን፡፡
የሙገር ፀሐይ የተለየች ሳትሆን አትቀርም፡፡ ጠፈር ላይ ያለች ሳትሆን አንዱ ዛፍ ላይ ተንጠልጥላ የምታቃጥል ነው የምትመስለው፡፡ የዛፎች ጥላ እንኳን አይመክታትም፡፡ ባገኘነው ዛፍ ሥር ሁሉ እየተጠለልን እርሷ ግን ድብብቆሽ እንደያዘ ሕፃን ብቅ ትልና ‹አየሁህ› ትለናለች፡፡
ከሁላችን ቀድሞ ዳገቱን እንደ አክርማ የሰነጠቀው ያሬድ ነው፡፡ እኛ ከኋላ ተስበን ነበር የገባነው፡፡ ገዳሙ ስንደርስ እማሆይ ተቀበሉን፡፡ ያንን ከተቆላ ስንዴ ዱቄት፣ በቅመም አዘጋጅተው የሚያፈሉትን ሻሂ ነበር ያቀረቡልን፡፡ እኔ ያንን ሻሂ በጣም ነው የወደድኩት፡፡ ያሬድማ ለሆቴሉ አስቦት ነው መሰል አጥብቆ አሠራሩን ሲጠይቃቸው ነበር፡፡
የተራራው መንገድ አላለቀም፡፡ ከዚህ በኋላ የአንድ ሰዓት መንገድ ወደ ወለንኮሚ ከተማ ይቀረናል፡፡ እዚሁ ጥቂት ጊዜ እንረፍና ገዳሙን በሙሉ ኃይላቸው የሚረዱትን የአዲስ አበባ የተክለ ሐዋርያት ማኅበርተኞችን እናመስግናቸው፡፡ እንዲህ ታሪክና እምነት ለመጠበቅ በረሃና ገደል የሚሻገር ወጣት ማግኘት ኩራት ነው፡፡ በአህያና በሰው ጫንቃ እያሸከሙ፣ እነርሱም ከቆንጥሩና ገደሉ ጋር እየታገሉ ነው አስደናቂውን የገደል ሥር ቤተ ክርስቲያን የሠሩት፡፡
|
ከወለንኮሚ ወደ እንጭኒ – በአይሱዙ
|
የሙገር በረሃ እጅግ ጥልቅ ጥናት የሚጠይቅ፣ ብዙ ነገሮችም ሳይጠፉ አሁንም ያሉበት ቦታ ነው፡፡ አሁን ፋብሪካዎቹ እየበዙ መልክዐ ምድሩና የሕዝቡ አሠፋፈር ከመቀየሩ በፊት ጥናቱ ይቀድም ዘንድ ደብረ ጽሞና ላይ ዐረፍ ብለን ሃሳብ እንሰጣለን፡፡ ምክንያቱም ከዚህ በኋላ አንድ ሰዓት የሚወስደውን ዳገት ከወጣን ሃሳባችንም ሊጠፋብን ይችላልና፡፡
© ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ የወጣ ስለሆነ በሌላ ሚዲያ መጠቀም ክልክል ነው