አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ማን ናቸው?

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስና አቡነ ተክለ ሃይማኖት(EMML 3051) 18ኛው መክዘ
አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በ13ኛው መክዘ ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ግብጻዊ ቅዱስ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መረጃዎች መሠረት ወደ ኢትዮጵያ ገቡ የሚባለው በዐፄ ላሊበላ ዘመን ነው፡፡ የትውልድ ቦታቸው በላዕላይ ግብጽ ንሒሳ   (የአሁኑ ባሕቢት አል ሐጋራ) ነው፡፡ [በርግጥ አንዳንድ ሊቃውንት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ኢትዮጵያዊ መሆናቸው፤ ነገር ግን የወላጆቻቸው ስም በሚገባ ለመታወቅ ባለመቻሉ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እናታቸው አቅሌስያ (ቤተ ክርስቲያን)፣ አባታቸውም ስምዖን (ካህን) እንደተባሉና የዚህም ምክንያቱ ከቤተ ክርስቲያን የተገኙ ለማለት መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ አንድ መጽሐፈ ታሪክም ‹አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወአቡነ ተክለ ሃይማኖት ብጹዐን ወቅዱሳን ተወልዱ በኢትዮጵያ› ይላል፡፡EMML 5538,f 55]
አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከ500 ዓመታት በላይ በዚህ ምድር ላይ መኖራቸውንና ከትግራይ እስከ ሸዋ ባለው ክፍል ተዘዋውረው ማስተማራቸውን፡፡ በዚህም ምክንያት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስንና ምድረ ከብድ ገዳማትን መትከላቸውን ታካቸው ያሳያል፡፡ ያረፉት በዐፄ ሕዝብ ናኝ ዘመን (1414-1418ዓም) ነው፡፡ ጻድቁ በትግራይ አቡዬ፣ በአማራው አቡነ፣ በኦሮሞዎች ዘንድ ደግሞ አቦ በመባል ይታወቃሉ፡፡ ዋናዎቹ ገዳሞቻቸው ሁለት ሲሆኑ ዝቋላ በኦሮምያ ክልል፣ ምድረ ከብድ ደግሞ በደቡብ ክልል ይገኛሉ፡፡ 

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን
1.      ከውጭ መጥተው ኢትዮጵያ ውስጥ ከኖሩ ቅዱሳን አንዱ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚታወቁት ቅዱሳን ከአመጣጣቸውና አኗኗራቸው አንጻር በሦስት ይመደባሉ፡፡ ኢትዮጵያ ተወልደውና ኖረው ኢትዮጵያ ያረፉ(አብዛኞቹ ቅዱሳን በዚህ ምድብ ናቸው)፣ ከውጭ መጥተውና ኖረው ኢትዮጵያ ያረፉ(ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ማኅበረ ጻድቃን፣ ተሰዓቱ ቅዱሳን፣ አባ ሊባኖስ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ እጨጌ ዕንባቆም) ኢትዮጵያ ተወልደው ውጭ ኖረው ያረፉ(አቡነ ኤዎስጣቴዎስ፣ ሙሴ ጸሊም፣ ሙሴ ሐበሻው(ሙሳ አል ሐበሽ)፣ገብረ ክርስቶስ(አብዱል መሲሕ))፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በውጭ ሀገር ተወልደው ኢትዮጵያ መጥተው ኖረው ካረፉት ቅዱሳን የሚመደቡ ናቸው፡፡
2 1በቁም ከሚሳሉ ጥንታውያን ሥዕሎች አንዱ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የግድግዳና የብራና ላይ ሥዕሎች መካከል ለብቻቸው በቁም በአብዛኞቹ አብያተ ክርስቲያናት ከሚሳሉት አራት ቅዱሳን (አቡነ ተክለ ሃይማኖት፣ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስና አቡነ አረጋዊ) አንዱ ናቸው፡፡ የቁም ሥዕላቸው ከወሎ ገነተ ማርያም እስከ አዲስ አበባ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ግድግዳ ላይ ይገኛል፡፡
3 2. ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቀጥለው በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚከበሩ ጻድቅ ናቸው፡፡ በ1990 ዓም በነበረው የሰበካ ጉባኤ የአብያተ ክርስቲያናት ቅጽ መሠረት በመላ ሀገሪቱ ከ2620 በላይ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ስም የሚጠሩ አብያተ ክርስቲያናት ነበሩ፡፡
4 3. የንጉሥ ዐዋጅ ቅድስናቸውን ካወጀላቸው ቅዱሳን አንዱ ናቸው፡፡ በዓላቸው በመጋቢትና በጥቅምት 5፣ በጥቅምት 27 እና በታኅሣሥ 29 እንዲሆን ንጉሥ ሕዝብ ናኝ ዐውጇል፡፡
5 4. በ14/15ኛው መክዘ የጸሎት መጻሕፍት የሥርዓተ ጸሎት ቅደም ተከተል መሠረት ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቀጥለው ለምልጃ የሚጠሩት ገብረ መንፈስ ቅዱስ ናቸው፡፡
6 5. በሰዓታትና ኪዳን ጸሎት ጊዜ ገድላቸው ከሚነበቡ ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን (አቡነ ተክለ ሃይማኖት፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ አቡነ አረጋዊ) አንዱ ናቸው፡፡
7 6. የአራዊት አባቶች ከሚባሉት(አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ፣ አቡነ አረጋዊ፣ አቡነ በርተሎሜዎስ) አንዱ ናቸው፡፡
አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በሕዝቡ ባሕል ውስጥ፤ ለምን?
አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን በተለየ በሕዝቡ ባሕል ውስጥ ቦታ አላቸው፡፡ በሕዝቡ ባሕል ውስጥ ቦታ በመያዝ ከቅድስት ድንግል ማርያም ቀጥሎ ያለውን ቦታ ሳይዙ አይቀሩም፡፡ የዚህን ምክንያት በርግጠኛነት መናገር ከባድ ይመስለኛል፡፡ የእኔ ግምት ግን ከሁለት ነገር የመነጨ ነው፡፡
1.      አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በሽምግልናቸው የሚታወቁ ጻድቅ በመሆናቸውና በኢትዮጵያውያን ዘንድ ሽማግሌ ካለው የከበሬታ ሥፍራ የመነጨ ሊሆን ይችላል፡፡
2.     ሲመጡ ከቅዱስ ላሊበላ፣ ሲያርፉ ከንጉሥ ሕዝብ ናኝ ጋር ከነበራቸው ግንኙነት ባለፈ ከቤተ መንግሥቱ ርቀው የኖሩ ሕዝባዊ አባት በመሆናቸው የተነሣ የተፈጠረ ሕዝባዊ ቅቡልነት ሊሆን ይችላል፡፡
ማሳያዎች
፩. በይትበሃሎች
1.      አስታራቂነት፡- ነብርና አንበሳ አይስማሙም፤ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሥዕል ሥር ግን ነብርና አንበሳ ተስማምተው ይታያሉ፡፡ በዚህ የተነሣ ለመታረቅ አስቸጋሪ የሆኑ ሰዎችን ለማስታረቅ የሚሄዱ ሽማግሌዎች ‹አቦን ሆነን መጥተናል› ይላሉ፡፡
2.     የአቦ ጠበል፡- አንድ ሰው እየተመገበ ቢያንቀው ‹የአቦ ጠበል› እያልክ ውኃን ሦስት ጊዜ ጠጣው ይባላል፡፡
3.     የአቦ ብቅል፡- አንድ ሰው ከማያውቀው ቦታ ስሙ ቢጠራና በአካባቢው የሚያውቀውን ሰው ቢያጣ የጠራው ሰይጣን ሊሆን ስለሚችል ‹‹የአቦን ብቅል እፈጫለሁ› በል ይባላል፡፡
4.     የአቦ መገበሪያ፡- አንድ ሰው አንድን ነገር አጥፍቶ ተሠውሮ እንደማይቀመጥ ለመግለጥ ‹‹የአቦን መገበሪያ የበላ ሲለፈልፍ ይውላል›› ይባላል፡፡
5.     አቦ ሰጥ፡- አንድ ሰው የማያውቀውን ነገር በግምት ሲናገር ‹አቦ ሰጥ› ይባላል፡፡
6.     በአቦ ይዤሃለሁ፡- አራዊት የቤት እንስሳትን እንዳይበሉባቸው ገበሬዎች ‹በአቦ ይዤሃለሁ› ብለው ይገዝቷቸዋል፡፡
7.     የአቦ መንገድ፡- በሰሜን ሸዋ መራኛ አካባቢ ባሉ ሕዝቦች ዘንድ ‹የአቦ መንገድ› የሚባል ብሂል አለ፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሚዳ ከሚገኘው የአቡነ መልከ ጼዴቅ ገዳም ጥቂት ጊዜ ቆይተዋል ይባላል፡፡ በኋላ ከዚያ ገዳም ሲወጡ አቡነ መልከ ጼዴቅ ‹‹የት ሊሄዱ ነው›› ብለው ቢጠይቋቸው ‹እርሱ ወደ መራኝ›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ከተማው ‹‹መራኛ›. የተባለው በዚህ ምክንያት ነው ይባላል፡፡ ታድያ በዚህ ምክንያት አንድ ሰው መድረሻውን በውል ሳያውቀው መንገድ ሲጀምር መንገዱ ‹የአቦ መንገድ› ይባላል፡፡
8.     የአቦ ቁራ፡- ሰይጣን በቁራ ተመስሎ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ዓይናቸውን ሊያወጣ ስለመጣ በጎ ነገር የያዘ መስሎ የሚመጣ ክፉ ሰው ‹የአቦ ቁራ› ይባላል፡፡
9.     በአቦ በሥላሴ፡- በሕዝቡ ብሂል ውስጥ ከሥላሴ ጋር ተያይዘው ብዙ ጊዜ የሚጠሩት ገብረ መንፈስ ቅዱስ ናቸው፡፡ ‹በአቦ በሥላሴ› ሲባል አጥብቆ መለመን ነው፡፡ በሕዝባዊ መዝሙሮችም ውስጥ ‹በአምስት አቦ ናቸው በሰባት ሥላሴ› የሚል ሐረግ በተደጋጋሚ ይሰማል፡፡
፪. በባሕላዊ ዘመን ቆጠራ
አቦ በገበሬው የወቅት አከፋፈል የዘመን መክፈያ ናቸው፡፡
1.      በገበሬው የዘመን ቆጠራ ክረምት የሚገባው ‹የሐምሌ አቦ› ዕለት ነው፡፡ የሚወጣው ደግሞ ‹የጥቅምት አቦ›፡፡
2.     በልግ ይገባል የሚባለው በየካቲት አቦ ስለሆነ ገበሬው ‹የካቲት አቦን አይተህ ተሰደድ› ይላል፡፡ በየካቲት አቦ ዝናብ ካልጣለ በልግ የለም ማለት ስለሆነ ሀገርህን ልቀቅ ነው፡፤
3.     በገበሬው ዘንድ የወሩ መግቢያ የአቦ ቀን ነው፡፡ ቀጠሮ ሲይዝ ‹አቦ በዋለ በዚህኛው ቀን› ብሎ ነው፡፡
      . አቦና ዐርበኛነት
የአቦ ቤተ ክርስቲያን ካህናት በአንኮበር፣ በጎንደርና በአዲስ አበባ ስማቸው ከዐርበኛነት ጋር ይነሣል፡፡ በሦስቱም ቦታ የሚገኙት የአቦ ቤተ ክርስቲያን ካህናት በአምስት ዓመቱ የጣልያን ወረራ በግልጽ አርበኞችን ደግፈዋል፣ ወደ በረሐ ወርደውም ታግለዋል፡፡ በዚህ ምክያትም ሦስቱም አብያተ ክርስቲያናት በጣልያን ዝርፊያና አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ የሦስቱም ካህናት ወደ በረሐ ሲገቡ የገጠሙት ግጥምም በሥነ ቃላችን ተላልፎ እኛ ዘመን ደርሷል፡፡
አንኮበር፡-
አቡዬን ብዬ እንጂ ይህን ሁሉ ማይ
አገሬ አይደለም ወይ ዠማና አዳባይ
ጎንደር
ፊት አቦ ጎንደር፡-
እንኳን እኔ ጀግናው የፊት አቦ ልጅ
ጎንደሬ ለጣልያን አይሰጠውም እጅ
ቀበና አቦ፣ አዲስ አበባ፡-
ወግጅልኝ ድጓ ወግጅልኝ ቅኔ
ወንዶች ከዋሉበት እውላለሁ እኔ
፬. ስምና አቦ
እስከ አሁን ድረስ ባለው ባሕል ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ድንግል ማርያም ስሞች ውጭ ስማቸው ስም የሚሆነው አቦ ናቸው፡፡ ‹አቦ ነሽ፣ አቦ ነህ› የሚል ስም አለን፡፡ በሌሎቹ ቅዱሳን ግን የለም፡፡ ዘርፍ ይጨመርበታል፡፡ ወለተ፣ ገብረ እንደሚለው ያለ፡፡
፭. አቦና ጠበል
የገጠር ሰው ትዳር ሲይዝ መጀመሪያ የሚጠጣው አቦን ነው፡፡ አቦን ቀድሞ የጠጣ ትዳሩ ይሠምራል፣ ከሰውም ጋር በሰላም ይኖራል ተብሎ ይታመናል፡፡
፮. አቦ የቅኔ መማሪያ
‹አቦ ቅኔ› ለቅኔ ተማሪ የመማሪያ ሁለት ቤት ቅኔ ነው
‹አቦ ውርዝው እምነ ኩሉ በለጡ
አንድ እንጀራ በጨው እስመ በማለዳ ለምጠጡ
ማጠቃለያ
ከላይ ያየናቸውን ሥነ ቃላውያን መረጃዎች መሠረት ስናደርግ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከሌሎች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን በላይ በሕዝቡ ውስጥ ባሕላዊ ቦታ እንዳላቸው ያሳየናል፡፡ የዚህ ምክንያቱ ምናልባት ‹ሽምግልናቸው› ሽምግልናን ከሚያከብረው ባሕላችን ጋር ተስማምቶ ወይም አብዛኛው ታሪካቸው ከቤተ መንግሥት የራቀ መሆኑ ሕዝባዊ ቅቡልነትን ስላስገኘላቸው ሊሆን ይችል እንደሆነ እንጃ፡፡ በዚህ ረገድ ከእርሳቸው የላቀ ባሕላዊ ቦታ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ያላት ቅድስት ድንግል ማርያም ናት(የማርያም መቀነት፣ የማርያም አራስ፣ የማርያም ፈረስ፣ የማርያም ግርዝ፣ ማርያም በሽልም ታውጣሽ፣ ማርያም ትቅረብሽ፣ ወዘተ)፡፡
ይህ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ባሕላዊ ቦታ ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን በእምነት ውስጥ ካላቸው ቦታ በተጨማሪ በሕዝቡ ውስጥ ያላቸውን ሀገራዊ ሥፍራ የሚያሳይ፣ እነርሱን በተመለከተ የምንሠራቸው ሥራዎች የት ድረስ የሕዝቡን ታሪካዊና ባሕላዊ መሠረት ጭምር ሊያንጹ ወይም ሊንዱ እንደሚችሉ ደግመን እንድናስብ የሚያመለክተን ማሳያ ነው፡፡ 
ላስ ቬጋስ፣ ኔቫዳ

(ያሬድ ሹመቴ)

አያልቅበት ስንታየሁ ሱዳን ውስጥ ለ3 ዓመት ያህል የኖረ የብርሀኑ ጌታነህ ወዳጅ ነው። የሚናፍቃቸውን እና ያላባት ብቻቸውን ያሳደጉትን፤ ለስደቱ ምክንያት የሆኑትን እናቱን ለማየት የዛሬ ዓመት ገደማ ወደ ሀገሩ ተመለሰ።

ሱዳን በነበረበት ወቅት ከራሱ ተርፎ እናቱን ለመርዳት የሚልካት ጥቂት ገንዘብ በስተርጅናቸው ሰው ቤት ተቀጥረው የጉልበት ስራ ከመስራት አላዳናቸውም።

ወይዘሮ አለሚቱ በላይነህ ልጃቸው ሱዳን ሳለ የሚልክላቸው ገንዘብ ከቤት ክራይ ክፍያ ውጪ የማይሸፍንላቸው ቢሆንም፤ ችግራቸውን ለልጃቸው ነግረው ከማሳቀቅ፤ በስተርጅናቸው የጉልበት ስራ ውስጥ ገብተው ኑሮዋቸውን በመከራ ተያይዘው ቆዪ።


የእናቱ ነገር የማይሆንለት አያልቅበት፤ በናፍቆቱ ምክንያት ወደ ሀገሩ ሲመለስ ግን ሱዳን እያለ ይልክ የነበረው ገንዘብ ምን ያህል የእናቱን ህይወት ፈቅ ማድረግ እንደተሳነው ተረዳ።
የዚያን ጊዜ ታድያ ከሱዳን አድማስ ማዶ፤ እናቱን ለመጦር ይችልበት ዘንድ ተስፋ የጣለበትን የባህር ላይ ጉዞ ህልም ሰነቀ።

ለልጆቹ ህይወት በእጅጉ ከሚጨነቀው የረዥም ጊዜ ወዳጁ ብርሀኑ ጌታሁን ጋርም ሀሳባቸው ገጠመ። ወደ ሊቢያም በጋራ ሊሻገሩ ተቃጠሩ። ልጆችን ለማሳደግና እናትን ለመጦር።
አያልቅበት በሀምሌ 5፣ 2007 ዓ.ም ወደ ሱዳን ለመመለስ በሚሸኝበት ጊዜ፤ ከዚህ ቀደም በሰላም ደርሶ የተመለሰው ልጃቸው ተመልሶ የሚመጣው መርዶው መሆኑን ፈፅሞውኑ ባይገቱም ካይናቸው ልጃቸው ከሚርቅ በርሀብ ቀድመውት ቢሞቱ መርጠው ነበር።

የብርሀኑ እና አያልቅበት ቀጠሮ ቀን ሲደርስ፤ ብርሀኑ ሚስቱን “ድሬዳዋ ለስራ መሄዴ ነው፤ ስልኬ ግን አይሰራም” ብሎ ሀገሩን ለቆ ወደ ሱዳን አመራ።

በተቀጣጠሩ በስድስት ወራቸው ሱዳን ላይ የተገናኙት እኒህ የልብ ወዳጆች፤ አንዳቸው ስለ ልጅ አንዳቸው ስለ እናት ፍቅር ምስክር ሆነው። ልጆቹን ለናታቸው አደራ ሰጥቶ የተሰደደው፤ ለእናት የሚሰጥ ፍቅር ሀያልነት በአያልቅበት ሲማር፤ ለልጆቹ ሲል የተሰደደው ብርሀኑ ደግሞ በተራው የአባት ፍቅር ምሳሌው ነበር።

ወይዘሮ አለሚቱ፤ አያልቅበት ከሄደ በጝላም ቢሆን የዘወትር ፀሎታቸው የሚወዱት ልጃቸው መንከራተት በቅቶት ከእቅፋቸው ዳግም እንዲገባ ነበር።

የሀገራችን ሰማይ ጠቁሮ፤ ኢትዮጵያም አምርራ በልጆችዎ የግፍ ሞት ስታለቅስ፤ እንደ ብርሀኑ ባለቤት ብርቱካን እና መላው ኢትዮጵያዊ ሁሉ የአያልቅበት እናትም እንባቸውን ይዘረግፉት ነበር። ሊቢያ የማን ሀገር ጎረቤት እንደሆነች እንክዋን የማያውቁት እናት እንዲሁ በደፈናው ልጆቼ ለሚልዋቸው የኢትዮጵያ ሰማዕታት ሁሉ ያነቡ ነበር።

ከሚወደው ወዳጁ ብርሀኑ ጎን በሊቢያ በርሀ አንገቱን ለሰይፍ የሰጠው አያልቅበት ሰማዕትነቱ የተሰማው ዘግይቶ የሁሉም ቤት ሀዘን በመብረድ ላይ ሳለ ነበር።

የእኒህን እናት አይን ለማየት በውነቱ ማን ይደፍር ይሆን? የሀዘናቸውንስ ጥልቀት ምን ይገልፀው ይሆን? በምንስ አይነት መንገድ….?

ዛሬም ቢሆን ስሜቴ ክፉኛ ተጎድቶአል። ገርጂ ከጊዮርጊስ ቤ.ክርስቲያን ጀርባ በምትገኘው ሰማዕቱ ልጃቸው በተከራየላቸው ጠባብ ቤት ውስጥ፤ በብቸኝነት ተኮራምተው፤ አንድያ ልጃቸው ተመልሶ እንደማያዪት ከተረዱ ሳምንት ሳይሞላቸው ያለ አስተዛዛኝ ብቻቸውን የተቀመጡት እናት፤ የሚያነጋግራቸው ዘመድ፣ ሲቦርቁ እያዪ የሚፅናኑባቸው ህፃናት የሌሉበት ጠባብ ቤት ያለመጠን ሰፍቶ ፍርሀት ሲያነግስባቸው፤ ቤታቸው የተሰቀለው ልጃቸውን ከነገዳዩ የሚያሳይ ምስል እያባነነ እንቅልፍ ሲከለክላቸው፤ ይህንን ሁሉ እየሰማን እና ይህን ሁሉ እያየን ዝም የምንል መሆናችን ያሳፍራል። (በእርግጥ ለህዝቡ ማን ነገረው? የመንግስት ሚድያዎች በሌሎች ጉዳዮች ተጠምደዋል።

ሀላፊነታቸውን በብርቱ ይወጡ የነበሩ ጋዜጦች እና መጵሄቶች ዛሬ በስራ ላይ የሉም) ዛሬስ እኔም እፍረት በዝቶብኝ አንቆ ሊደፋኝ ደርሶዋል።

አያልቅበት እኮ “የሞተው ሁላችንንም ተክቶ ነው። እሱ እኮ አንገቱን የደፋው የናቱን አንገት ቀና ሊያደርግ ነው።”

በኢትዮጵያ አምላክ እለምናለው አዛውንት እናትና ህፃናት ልጆች አንድ ናቸው። ስደቱም የመጣው ለማሳደግና ለመጦር ነው። እኚህን እናት አጠገባቸው ሄደን እናጽናናቸው። ቀሪ ህይወታቸውንም ወድቀው እንዳይቀሩ እንደግፋቸው።

የሰማዕቱ አያልቅበት ድምጽ ግን ይሰማል። ብቸኛዋን “እናቴን አደራ”።

ለሰማዕቱ አያልቅበት ነፍስ ይማርልን!! እንፀድቅባቸው ዘንድ እናቱንም ትቶልን ከሱ ሰማዕትነት
በረከት እንድንሳተፍ እነሆ “እናቴን አደራ” ይለናል።

ከቻሉ በአካል ተገኝተው እናታችንን ያፅናኑ፤ ካልቻሉ ይህን መልዕክት share በማድረግ የሰማዕታቱ ቤተሰቦች መሆናችንን (እንግለጥ።)

አሁንም በድጋሚ እናገራለው። ከብዙ ቃል መግባት ጥቂት ቃልን መፈፀም ዋጋው የላቀ ነው። እግዚአብሔር ይርዳን!!

በግፈኛው አይሲስ ከተሠዉት ወንድሞች መካከል ብርሃኑ ጌታነህ የተባለው በአዲስ አበባ አቧሬ አካባቢ ይኖር የነበረው ወንድም ይገኝበታል፡፡ ብርሃኑ ከሀገሩ የወጣው ከአራት ወራት በፊት ሲሆን ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ነበረ፡፡ ቤተሰቦቹ እንደሚናገሩት ወደ ሱዳን ሲሄድ ለባለቤቱ የ3 ወር የቤት ኪራይ ከፍሎ ነበር የሄደው፡፡ ሁለቱ ልጆቹ የስምንትና የአራት ዓመት እድሜ ያላቸው ሲሆኑ ቤተሰቡ በችግር ላይ እንደሚገኝ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተለው መሐመድ ካሣ ማክሰኞ ምሸት ወደ አሜሪካ ልበር ስል ነግሮኝ ነበር፡፡ እስካሁን መርዶ የተረዱት የሰማዕታቱ ቤተሰቦች ወላጆች፣ እኅቶች ወይም ወንድሞች ሲሆኑ ብርሃኑ ግን ባለቤቱና ገና ክፉና ደግ ያልለዩት ሁለቱ ልጆቹ ናቸው የተረዱት፡፡

ፎቶ፡- ያሬድ ሹመቴ

ከሰማዕታቱ ቤተሰቦች መካከል ይበልጥ ትኩረት የሚፈልጉት እነዚህ ምንም የማያውቁ ሕጻናትና እናታቸው ናቸው፡፡ መማር፣ ተምሮም ማደግ አለባቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ መኖሪያ ቤትና የትምህርት ቤት ክፍያ ይፈልጋሉ፡፡ እናታቸውንም በሥራ ማሠማራት ይጠይቃል፡፡ በመሆኑም የክፉዎቹ ሥራ ውጤት እንዳይኖረው እነዚህን ሁለት ሕጻናትና እናታቸው እንርዳ፡፡ ቤታቸው አቧሬ አድዋ ድልድይ አካባቢ ነው፡፡  

ጉዳዩን በሚገባ ለመረዳትና ርዳታውን ለማስተባበር መሐመድ ካሣን ብታነጋግሩት ያግዛችኋል፡፡ ስልኩ 0911602795 ነው፡፡
ዳላስ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ዋሽንግተን ዲሲ

‹ጀማል› የተባለ ሙስሊም ወንድማችን በሊቢያ ከተሠዉ ክርስቲያኖች ጋር አብሮ ተሠዉቷል እየተባለ ሲነገር ቆይቷል፡፡ በአካባቢው የነበሩ የዓይን እማኞችና ሌሎችም የቅርብ ምንጮች ታሪኩ የተሳሳተ መሆኑን ቢናገሩም ሰሚ ለማግኘት ግን አልተቻለም፡፡ አንዳንዶቹም ታሪኩን የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችና ክርስቲያኖች ፍቅር ማሳያ አድርገው ተሟግተዋል፡፡ እንደ እኔ ግን ይህንን ታላቅ ፍቅር ለማሳየት ‹ጀማል› የተባለ መሥዋዕት መፍጠር አያስፈልገንም፡፡ ፍቅሩ  ነበረ፤ አለ፡፡ ተጨማሪ ፈጠራው አያስፈልገውም ነበር፡፡

‹ጀማል› ነው ተብሎ ሲነገርለት የነበረው ወንድማችን ግን ኤፍሬም የተባለ ኤርትራዊ፣ ቃኘው ሠፈር ይኖር የነበረ ክርስቲያን ነው፡፡ ቤተሰቦቹ ሁለት መርዶ እንደመጣባቸው እየገለጡ ነው፡፡ በአንድ በኩል በአሰቃቂ ሁኔታ በአይሲስ መሠዋቱ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ‹ሙስሊም› ነው መባሉ ነው፡፡ 

ኖርዌይ የነበሩ ኤርትራውያን ክርስቲያኖች ወዲያው ነበር ነገሩን የተቃወሙት፡፡ ነገር ግን አሥመራ ያሉት ቤተሰቦቹ እስኪረዱ ድረስ ትክክለኛ ስሙን ለመግለጥ አልተፈለገም፡፡ በዚህ መዘግየት የተነሣም ብዙ የፈጠራ ታሪኮች ተፈጠሩ፡፡ አንዳንድ የማኅበራዊ ሚዲያ አቀንቃኞች በላኩልኝ የውስጥ መልእክት የጀማልን ሙስሊምነት መካድ ሙስሊሞች ለክርስቲያኖች ያላቸውን ድጋፍና ፍቅር መካድ ነው ሲሉ ገልጠዋል፡፡ ለእኔ ግን ከተፈጠረው ‹ጀማል› ይልቅ እዚሁ አዲስ አበባ ያለው መሐመድ ካሣ ይህንን ልዩ ፍቅር ከንጋት ኮከብ በላይ አጉልቶ አሳይቶኛል፡፡ ልቡ እስኪደክም ኀዘንተኞቹን ለማጽናናትና ለመርዳት የሚደክመው፤ ለምን ጉባኤ አይደረግም፣ መዘምራን ለምን አይመጡም፣ መምህራን ለምን አያስተምሩም እያለ ልቅሶ ቤቶቹን ከክርስቲያኖቹ በላይ ሲያገለግል የነበረው፤ ተዝካራቸው መውጣት አለበት ብሎ ከካህናቱ ጋር የሚሟገተው፣ ድንበር ተሻጋሪውና ድልድይ ገንቢው መሐመድ ካሣ ለኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችና ክርስቲያኖች ፍቅር ከበቂ በላይ ማሳያዬ ነው፡፡ ያየሁት፣ የነካሁት፣ የበለጠኝ ማስረጃዬ፡፡ ፈጠራ አያስፈልገኝም፡፡
ኤፍሬም ሆይ በረከትህ ይደርብን፡፡

ዳንኤል ክብረት
ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓም
ባሕርዳር
ለባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ተቋም ምሥረታ ማብሠሪያ ቀን የቀረበ የማሳሰቢያ ሐሳብ
ዩአን ሊ የተሰኘ ጃፓናዊ Breaking the message, በተሰኘው የ2006 ዓም መጽሐፉ ላይ እንዲህ ይላል፡፡ በኢንዶኔዥያ ገጠሮች ውስጥ በሠራባቸው 7 ዓመታት የታዘበው ትልቁ የሕዝብ ግንኙነት ችግር ለሕዝቡ መልእክት ለማስተላለፍ የሚመጡት ባለሞያዎች መልእክታቸው ተሟልቶ ወደ ሕዝቡ ለመድረስ አለመቻሉ ነው፡፡ ለዚህ ችግር መፈጠር ምክንያት ናቸው ያላቸው ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ የመጀመሪያው መልእክቱ ለሕዝቡ በሚመጥን መልኩ ተዘጋጅቶ አለመቅረቡ ነው፡፡ የሚተላለፈው መልእክት የአስተላላፊውን ማንነት፣ የዕውቀት ደረጃ፣ የፖለቲካ ጠገግ፣ የተማረውን የትምህርት ዓይነትና የአስተሳሰቡን መጠን የሚያሳይ እንጂ ለመልእክት ተቀባዩ ታስቦ በደረጃውና በመጠኑ የቀረበ አይደለም፡፡
‹‹ምንም እንኳን ሥጋ ሥጋ ቢሆንም ለሕጻንና ለዐዋቂ ግን በእኩል መጠንና ዓይነት አይቀርብም፡፡ ሕጻኑ ጥርሱና የምግብ ማዋሐጃ አካሉ ስላልጠነከረ በቀላሉ ሊፈጨው በሚችለው መጠን ሥጋው ደቅቆ መቅረብ አለበት፡፡ ለዐዋቂው ግን ሥጋው ጠንክሮና በቅመማ ቅመም ዳብሮ ሊቀርብ ይችላል፡፡ ሥጋ ግን ሥጋ ነው›› ይላል ዩአን ሊ፡፡ መልእክት ሲቀርብም ከአቅራቢው በላይ የሚቀርብለትን ወገን ዐቅምና ችሎታ፣ ደረጃና ፍላጎት የመጠነ መሆን አለበት፡፡ ምንም የመልእክቱ ይዘት ባይቀየርም፡፡ 

ሌላው ለመልእክቱ መሰበር ምክንያት ነው ብሎ የታዘበው ነገር ምሁራኑና ሌሎችም ሕዝቡ በማይገባው ቋንቋ መናገራቸው ነው፡፡ አቅራቢዎቹ ለምዶባቸው ወይም እነርሱ የተማሩት በእንግሊዝኛ በመሆኑ ያለበለዚያም (እንደ እኛ ሀገር የኛ ሙሽራ ኩሪባቸው በእንግሊዝ አናግሪያቸው የሚለው ዘፈን እነርሱም ጋር አለ መሰል) እንግሊዝኛ መቀላቀል የዕውቀትና የደረጃ ማሳያ አድርገውት፣ እንግሊዝኛውን ከኢንዶኔዥያ ቋንቋ ጋር (በነገራችን ላይ ኢንዶኔዥያ 700 ሀገራዊ ቋንቋ የሚነገርባት ሀገር ናት፤ ብዙዉ ሰው ‹ባሐሳ ኢንዶኔዥያ› የተሰኘውን ብሔራዊ ቋንቋ ይናገረዋል፡፡) እየቀላቀሉ በሚያስፈልገውም በማያስፈልገውም ስለሚጠቀሙ መልእክቱ እየተሰበረ እንዲደርስ አድርገውታል፡፡
‹‹በቴሌቭዥን ኳስ ስንከታተል›› ይላል ዩአን ሊ ‹‹የኳሱን ፍሰት ሳይቋረጥ መከታተል እንፈልጋለን፡፡ የቴሌቭዥን ጣቢያው  ይኼንን ትቶ በየመካከሉ ሙዚቃ እየጋበዘ ኳሱን ቢያስተላልፍልን የኳስ ጨዋታው ሙሉ ሥዕል አይኖረንም፡፡ ምናልባትም በመካከል ጎል ገብቶ፣ ተጨዋች በቀይ ወጥቶ፣ ግጭት ተፈጥሮ፣ ተጨዋች ተቀይሮ፣ አስደናቂ ወይም አሳዛኝ ክስተት ተፈጥሮ ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህን ነገሮች አሳልፈን የምናየው ጨዋታ ግርታን ይፈጥራል እንጂ ደስታን አያመነጭም፡፡ በየመካከሉ ሕዝቡ የማይረዳውን ቋንቋ እየደባለቁ መልእክት ለማስተላለፍ መጣርም እንደዚሁ ነው፡፡ ድምፁን ለማስተላለፍ እንጂ መልእክቱን ለማስተላለፍ አይረዳም›› ይላል፡፡
እንዲያውም በአንድ በሰሜናዊ ኢንዶኔዥያ ክፍል ጥናት ሲያደርግ አንድ አዛውንት የነገሩትን እንደ ምሳሌ አስቀምጦታል፡፡ በዚያ መንደር ውስጥ አንድ የሕክምና ባለሞያ መጥቶ ለመንደሯ ሰዎች ስለ ኢንፍሉዌንዛ ገለጻ ያደርጋል፡፡ በገለጻው መካከል የአካባቢውን ቋንቋ ሱንዳኒዝንና እንግሊዝኛን እየደባለቀ ይናገር ነበር፡፡ መንደርተኞቹ ተቸገሩ፡፡ አንድ ሰውም ተነሡና ‹ልጄ፣ ወይ በእንግሊዝኛ ንገረንና ከመካከላችን ዕውቀቱ ያላቸው ይተርጉሙልን፤ ያለበለዚያ ደግሞ በአካባቢያችንን ቋንቋ በሱንዳኒዝ ንገረንና ያለ ችግር እንስማው›› ብለው አስተያየት ሰጡት፡፡ ከባለሞያው ይልቅ መንደርተኞቹ እንደሚቆራረጥ ስልክ መልእክቱ እየተሰበረ እንደደረሳቸው ገብቷቸዋል፡፡
አሁን አሁን በሀገራችን እየገጠመን ያለውም ልክ ዩአን ሊ በኢንዶኔዥያ የገጠመውን ዓይነት ነው፡፡ አማርኛን የሚናገር ሰው የጠፋ እስኪመስል ድረስ በአማርኛ መልእክት መለዋወጥ ከባድ እየሆነ ነው፡፡ የመልእክት ልውውጦቻችን በስሕተቶች የ&#4720

እነዚህ ወገኖቻችን ሰማዕታት ናቸው፡፡ ሃይማኖታቸውን አንለውጥም ብለው የተሠዉ፡፡ ‹ስደተኛ ኢትዮጵያውያን› የሚለውን አገላለጽ ነፍሴ ትጸየፈዋለች፡፡ ከአኩሪው የሰማዕትነት ተግባራቸው በላይ ስደተኛነታቸው ለማጉላት ስለሚያኮበኩብ፡፡ ሰው በሀገሩ ቢኖር፣ ቢሠራና ቢከብር የመጀመሪያ ምርጫው ነው፡፡ በተለይ ኢትዮጵያውያን፡፡ ነገር ግን ‹እልፍ ሲሉ እልፍ ይገኛል› ይባላልና የቸገረው ቢሰደድ ምን ይፈረድበታል? በርግጥ ስደቱ በሰላም፣ በሕግና በጤና ቢሆን የማይወድ የለም፡፡ ግን ሁል ጊዜ ይቻላል ወይ? ምቹ ሁኔታስ አለ ወይ? ዛሬ ከአውሮፓ፣ አሜሪካና አውስትራልያ፣ ከአፍሪካና እስያ ገንዘባቸውን እየላኩ አንዳንዴ ከቡና በላይ አንዳንዴም ከቡና ቀጥሎ የውጭ ምንዛሬውን የሚያስገኙልን ወገኖች አብዛኞቹ ዛሬ ‹ሕገ ወጥ› በምንለው መልኩ የሄዱ አይደለም ወይ? እንዲያ እንዲሆኑ ያደረጋቸውን መሠረታዊ ምክንያት መፍታት እንጂ የሆኑበትን መንገድ ማውገዝ ምን ይጠቅማል? 

 

በሀገራችን ኢትዮጵያ እየኖሩ በአክራሪዎችና አሸባሪዎች ሕይወታቸው የተሠዉ ክርስቲያኖች አልነበሩም ወይ? በ1980ዎቹ መግቢያ በአሰቦት ገዳም የታረዱት መነኮሳት፣ በአርሲ ኮፈሌ የተገደሉትን ምእመናንና በ1998 ዓ.ም. በጅማ በሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተሠዉት ምእመናንና ካህናት ስደተኞች ሆነው አልነበረምኮ? ክርስቲያን ስለሆኑ እንጂ፡፡ በአይሲስ እጅ ወደቀው ከነበሩት መካከልኮ እነርሱ የእስልምና እምነት ይከተላሉ ብለው ያሰቧቸውን ሱዳናውያንና ሶማልያውያንን ያለ ምንም እንግልት ይለቋቸዋል፡፡ የቁርዐን ጥያቄ የሚጠየቁት ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ናቸው፡፡ ከእነርሱም መካከል ሙስሊም አይደለም ብለው ያሰቡትን ነው በኮንቴይነር አስገብተው ወደ አልታወቀ ሥፍራ የሚወስዱት፡፡ እነዚህም ቢሆኑ ምርጫ ይቀርብላቸዋል፡፡ ‹እስልምናን ወይንም ሞትን መቀበል› እምነታችንን አንለውጥም ሲሉ ይገደላሉ፡፡ አይሲስ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ክርስቲያኖችን ሲያርድ በግድ እንዲመለከት የተደረገው ኤርትራዊው የ16 ዓመት አዳጊ ወጣት ናኤል ጎይቶም ከእጃቸው አምልጦ ከወጣ በኋላ ለኢንተርናሽል ቢዝነስ ታይምስ የነገረውም ይሄንኑ ነው፡፡ ለቪኦኤ ቃሉን የሰጠው ከሞት ያመለጠ ወጣት ይህንኑ ያረጋገጠ ነበር፡፡ አይሲስም በአድራሻ ‹ጠላታችን ለሆነቺው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን› ብሎ ተናግሯል፡፡ አይሲስ ራሱ ሀገራዊ ብሔርተኝነትን ሳይሆን ሃይማኖታዊ ብሔርተኝነትን ማስፈን ነው  ዓላማው፡፡ ሊመሠርትም የተነሣው ‹የእስልምናን መንግሥት› ነው፡፡
ይኼ ሁሉ የሚያሳየው እነዚህ ወንድሞቻችን የተሠዉት ክርስቲያን በመሆናቸው እንደሆነ ነው፡፡ በንግግራችንም ሆነ በመግለጫችን ልንናገረው የሚገባን እውነትም ይኼው ነው፡፡ ሕገ ወጥ ስደትን እንኳን እኛ ስደተኛው ራሱም አይፈልገውም፡፡ የሞታቸው ዋና ምክንያት ግን ስደት አይደለም፡፡ ያ ቢሆን አብረዋቸው የተሰደዱት ሶማልያውያንና ሱዳናውያንም ይገደሉ ነበር፡፡ ምክንያቱ ክርስትናቸው ነው፡፡ እነርሱን ‹ባይሄዱ ኖሮ አይገደሉም ነበር› በሚል ዓይነት ጥፋተኞች ለማድረግ ለምን እንደክማለን፡፡ እነርሱ የአቋም ሰዎች ናቸው፡፡ ዘላቂውን አቋም ለጊዜያዊ ጥቅም መቀየር ያልፈቀዱ፡፡
ስለ እነዚህ ወንድሞች ክርስትና መናገር ሌሎች አማኞችን ያስቀይማል ወይም ያገላል ብለን ከሆነ ስሕተት ነው፡፡ ሙስሊሞችና ሌሎችም ወገኖቻችን ‹ማንም በእምነቱ ምክንያት መገደሉን እናወግዛለን› እያሉኮ ነው፡፡ የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ርእሰ መንበር ‹በዲናችን አስተምሮና አሳምኖ እንጂ አስገድዶና ገድሎ እምነት ማስቀየርን አንቀበልም› ነው ያሉት፡፡ ይኼ ነገር እነዚህ ወገኖቻችን በግድ እምነታችሁን ቀይሩ ተብለው በአረመኔዎች መገደላቸውን እየነገሩን ነው፡፡
ከአይሲስ እጅ በእግዚአብሔር ቸርነት ለወሬ ነጋሪነት ያመለጡ ወገኖች እንደሚናገሩት አይሲስ ትልቁ ትኩረቱ በኢትዮጵያና ኤርትራ ስደተኞች ላይ ነው፡፡ ሱዳናውያንንና ሶማልያውያን ወዲያው ነው የሚለቀው፡፡ በተለይ ደግሞ የመስቀል ምልክት በሰውነታቸው ላይ የተነቀሱና ሌሎች ሃይማኖታዊ ምልክቶችን ያደረጉትን ወዲያው ያለምንም ጥያቄ ክርስቲያን መሆናቸው አረጋግጦ ለብቻ በኮንቴይነር ያስቀምጣቸዋል፡፡ ከአይሲስ ጋር የሚደረግ ውይይት፣ ድርድር፣ ክርክር የለም፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የለበሱት የሊቢያ ወታደሮችን ልብስ ስለሆነ እነማን እንደሆኑ የሚታወቀው በኋላ ነው፡፡ የሰዎችን ጥያቄና ልመና ለማስተናገድ ዕድል የሚሰጡ አይደሉም፡፡
ከዚህ አንጻር ከኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ጋር ጀማል የተባለ ሶማልያዊ ሙስሊም ‹ክርስቲያኖችን እረዳለሁ ብሎ› አብሮ ተሠውቷል የሚለውን መረጃ ለመቀበል ይቸግራል፡፡ በመጀመሪያ ሶማልያውያንን ለጥያቄ አያቀርቧቸውም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ጓደኞቼን ትቼ አልሄድም ስላለ አይሲስ ‹ና አብረሃቸው ሂድ› ብሎ አስተያየት የሚያደርግ ቡድን አይደለም፡፡ በሌላ በኩል ተጓዦቹ ሲያዙ የሊቢያ ወታደሮች እንደያዟቸው እንጂ አይሲስ መሆናቸውን የሚያውቁበት ዕድል የለም፡፡ የለበሱት የወታደር ልብስ ነው፡፡ የመጀመሪያው መለያየት የሚፈጠረው ደግሞ እምነትን ሳይሆን ዜግነትን መሠረት አድርጎ ነው፡፡ ሶማልያውያንና ሱዳናውያን ወዲያው ያስኬዳሉ ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያን ይይዛሉ፡፡ ሶማልያውያንና ሱዳናውያን የሚይዙት የተለየ እምነታቸውን የሚጠራጥር ነገር ካገኙባቸው ብቻ ነው፡፡ እንደ ማተብ፣ የመስቀል ንቅሳት፣ የአለባበስ ለውጥ ወዘተ፡፡ ክርስትና ጥያቄ ሆኖ የሚመጣው ከዚያ በኋላ ነው፡፡ በኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ዘንድ፡፡
በዚህ ሁሉ ነገር ጀማል ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን ለመርዳት ዕድል የሚያገኝበት መንገድ የለም፡፡ ቢፈልግ እንኳን፡፡ እርሱ ከሶማልያውያን ጋር መጀመሪያ ተለይቶ ወይ ሄዷል፤ ወይ ሌላ ቦታ ተቀምጧል፡፡ እስካሁን ለማምለጥ ዕድል ያገኙ ወገኖችም ይህንን ታሪክ አያውቁትም፡፡ መረጃውን ሰጡ የተባሉት የሶማልያ ምንጮች ናቸው፡፡ ተርፈው የወጡ ወገኖች የሚጠራጠሩት ሁለት ነገር ነው፡፡ አንድ ጀማል እምነቱን ቀይሮ ክርስቲያን ከሆነና ይህንንም ከመሰከረ፤ ሁለት በሰውነቱ ላይ የመስቀል ንቅሳት አሠርቶ ከሆነ፡፡ ከዚያ ውጭ ግን ሶማልያዊ ሙስሊም ሆኖ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚታረድበት በቂ ምክንያት ሊኖር አይችልም፡፡ እንኳን ለመታረድ አብሮ ለመቆየት ዕድል የለውም፡፡  
ይኼ ማለት ሙስሊሞች ክርስቲያኖችን አይወዱም ወይም አይረዱም ማለት አይደለም፡፡ በሊቢያ ተደብቀው የሚገኙ ኢትዮጵያውያን መረዳዳቱን በሚገባ መስክረዋል፡፡ ይኼ የማይታበል ሐቅ ነው፡፡ ይኼ ነገር በራሱ ቆሞ ሊናገር የሚችል ስለሆነ ሌላ ነገር መፍጠር የሚያስፈልገው አይመስለኝም፡፡
ጀማልን በተመለከተ የተሠራጨውን ዜና መቶ በመቶ አይሆንም ማለት አይቻልም፡፡ በቦታው የለንምና፡፡ ከዓይን ምስክሮችና በሊቢያ ምድር ከሚገኙ ምንጮች፣ ተርፈውም ለመገናኛ ብዙኃን ምስክርነት ከሰጡ ሰዎች ተነሥተን ስናየው ግን ‹ተረጋግጦ ያለቀ እውነት ነው› ብሎ ለመቀበል የበለጠ መረጃ የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡   
እነዚህን ወገኖች ለማሰብ፣ ቤተሰቡን ለማጽናናት በቀጣይም ተመሳሳይ ነገር እንዳይከሰት ለመሥራት ቤተ መንግሥት፣ ቤተ ክህነት፣ ሚዲያዎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የንግድ ተቋማትና ሌሎችም እያደረጉ ያለው ነገር ነገሩን በኢትዮጵያዊ ባሕልና ወግ መሠረት ለማከናወን የሚደረገውን ጥረት ያሳያል፡፡ በየእምነት ተቋማቱ ጸሎት እየተደረገ ነው፡፡ በየ አጥቢያው ምሕላ እየተከናወነ ነው፡፡ በኀዘንተኞቹ ቤት ሕዝቡ በነቂስ እየተገኘ ኀዘኑን እየተካፈለ ነው፡፡ ኀዘንተኞቹም በሕዝቡ አጋርነት እየተጽናኑ ነው፡፡ ፓርላማው ያወጀው የሦስት ቀን ብሔራዊ ኀዘን እየተተገበረ ነው፡፡ የሚስመሰግን ነው፡፡
የምናደርጋቸው ነገሮች ግን እምነቱንና ትውፊቱን፣ ወጉንና ባሕሉን፣ ኅሊናንና ሰብእናን የጠበቁ ቢሆኑ መልካም ይሆናሉ፡፡ ርዳታችን፣ ኀዘናችን፣ ማጽናናታችን፣ ችግሩን ለመፍታት መሯሯጣችን እምነት፣ ኅሊና፣ ባሕልና ወግ አስገድዶን እንጂ ለተወዳጅነትና ለገጽታ ግንባታ ባይሆን ይመረጣል፡፡ የወገኖቻችንን መሥዋዕትነት ለፖለቲካ ጥቅም፣ ለሚዲያ ፍጆታ፣ ሩኅሩኅነታችንን ለማሳያ፣ ለጋስነታችንን ለማስመስከሪያ እንድንጠቀምበት ኢትዮጵያዊ ባሕልና ወግ አይፈቅድልንም፡፡ የምንሰጠው ገንዘብ፣ የምንወስደው የእዝን እንጀራ፣ የምንደርሰው ልቅሶ ሁሉ እየተቀረጸ፣ በፎቶ እየተነሣ፣ በሬዲዮ እየተላለፈ የሚደረግ ከሆነ ለራሳችን ገጽታ ስንል እንጂ አዝነን ያደረግነው መሆኑን ያጠራጥራል፡፡ ሌሎች ስለ እኛ ይናገሩ እንጂ እንዴት ‹ይህን አድርገናል፣ ይህን ሰጥተናል› እያልን ራሳችንን ራሳችን እንቀርጻለን፣ ራሳችንንስ እንዴት ራሳችን እናስተዋውቃለን? ነውር ቀረ ማለት ነው? የንግድ ድርጅቶችና ‹ታላላቅ ሰዎች› ይህንን ለራስ መክበሪያነት ሲያውሉት ማየት ግን ያማል፡፡
አንዳንድ ሰዎችን አይተናል ረድተዋል፣ ልቅሶ ደርሰዋል፣ አጽናንተዋል፣ የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል፡፡ ነገር ግን ነጋሪት እየጎሰሙ አይደለም፡፡ በርግጥ በተራራ ላይ ያለች መብራት ልትሠወር ስለማይቻላት ሌሎች አይተዋቸው ስለ እነርሱ ዘግበዋል፡፡ እነርሱ ግን ‹እዩልን ስሙልን› አላሉም፡፡ ‹አምስት ሺ ብር ሰጠሁ፣ ዐሥር ሺ ብር ሰጠሁ› ሲሉ አልተሰሙም፡፡ ድርጊቱን የተደረገለትና ዋጋ ቆጣሪው አምላክ ያውቀዋል፡፡ በሚዲያ ገብተውም ‹እገሌ ይህንን ያህል ሺ ብር ስለሰጠዎት አመስግኑት› ብለው የኀዘንተኛ ምስጋና አልሰበሰቡም፡፡
ጎበዝ እየተስተዋለ እንጂ፤ አንገቱን ለሰጠ ገንዘብ ሰጥን ብለን ይሄ ሁሉ ነጋሪት?
  

አሁን ከማልታ ባገኘሁት መረጃ በቀደም ከተሠዉት ወንድሞቻችን ጋር የነበረ ፣በእግዚአብሔር ቸርነት አምልጦ ትሪፖሊ የገባ ወንድም አግኝቼ ነበር፡፡
 

እርሱ እንደነገረኝ በአጅዛቢያና ቤንጋዚ መንገድ ላይ የአይሲስ አራጆች የሊቢያ መንግሥት ወታደሮችን ዩኒፎርም  ለብሰው በዚያ የሚያልፉትን ለመያዝ ይጠብቃሉ፡፡ በአካባቢው ወደ ትሪፖሊ የሚጓዙ መንገደኞችን ሲያገኙ ይይዛሉ፡፡ ሱዳኖችንና ሶማልያውያንን ሙስሊሞች ናቸው ብለው ስለሚያስቡ ወዲያው እንዲሄዱ ይለቋቸዋል፡፡ ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያንን ግን ለብቻ ይይዛሉ፡፡ ከዚያም ሙስሊሞችን ለብቻ ክርስቲኖችን ለብቻ ያሰልፏቸዋል፡፡ በመቀጠልም ክርስቲያኖችን በኮንቴይነር ውስጥ ከትተው ወዳልታወቀ ሥፍራ ይወስዷቸዋል፡፡ ሙስሊሞችን ደግሞ ይለቋቸዋል፡፡

በቀደም ዕለት አይሲስ በባሕር ዳርቻ የሠዋቸው ክርስቲያኖች በሰውነታቸው ላይ የመስቀል ምልክት የነበረባቸውን መርጦ ነው፡፡ እነርሱን በተለየ ኮንቴይነር አስቀምጧቸው ነበር፡፡ ይኼንን መረጃ የነገረኝ ሰው ሊገደሉ ተመርጠው ከተለዩት ወገን ነበረ፡፡ ሌሎች በኮንቴይነር ያስቀመጣቸው ክርስቲያኖችም አሉ፡፡ ምናልባት ከዚህ የከፋ ዜና እንሰማ ይሆናል፡፡ አምላክ ይጠብቀን፡፡ አሁንም የአይሲስ አራጆች የመንግሥት ወታደሮችን ልብስ ለብሰው ሌሎች ስደተኞችን እየያዙ ነው፡፡

ይኼ መረጃንውን ያደረሰኝ ሰው ሊያመልጥ የቻለው ሌሎች ክርስቲያኖችን በጨለማ ወደ ኮንቴይነሩ ለማስገባት ኮንቴይነሩን በከፈቱበት ጊዜ ነው፡፡ የተወሰኑ ተያዦች አምልጠው ነበር፡፡ አንዳንዶች ተያዙ፡፡ ሦስቱ ግን አመለጡ፡፡ ሁለቱ የት እንደደረሱ አያውቅም፤ እርሱ ግን በእግዚአብሔር ቸርነት አምልጦ ትሪፖሊ ገብቷል፡፡
እባካችሁ ባገኛችሁት አጋጣሚ ሁሉ ሰሞኑን ለመጓዝ የተነሡት ቢያንስ ለጊዜው ይታገሡ፡፡ ሱዳን ያሉትም ከሱዳን አይውጡ፡፡ መንገዱ በአይሲስ አራጆች ተይዟል፡፡ ለማታለልም የመንግሥት ወታደሮችን ልብስ ለብሰው ድንበር ጠባቂ ይመስላሉ፡፡
እግዚአብሔር በእጃቸው የተያዙትን እንዲታደግ እንጸልይ፡፡

Ethiopian martyrs in Libyaበተለያዩ የባለ ሥልጣናትና የእምነት መሪዎች መግለጫዎች ላይ በሊቢያ ምድር የተሠዉትን ሰማዕታት በኢትዮጵያዊነታቸው ወይም በስደተኛነታቸው ብቻ አደጋ እንደደረሰባቸው ተድርጎ እየተነገረ ነው፡፡ እነዚህ ክቡራን ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ የተሠዉትም እምነታቸውን አንለውጥም ስላሉ ነው፡፡ አይሲስ የሠዋቸው በኢትዮጵያዊነታቸው አይደለም፡፡ አይሲስኮ ዜግነት የለውም፡፡ ዐረቦች፣ አውሮፓውያን፣ አፍሪካውያን እስያውያን የተቀላቀሉት አሸባሪና አሰቃቂ ድርጅትና አስተሳሰብ ነው፡፡ እንዲያውም ባለፈው ሰሞን ትውልደ ኢትዮጵያውያን ከእንግሊዝ ወደ አይሲስ ለመግባት ያደረጉትን ጥረት በመገናኛ ብዙኃን ሰምተን ነበር፡፡ አይሲስ አገር የለውም፡፡

እነዚህ ወንድሞቻችንማ ማተብ የሚያደርጉበትን አንገት ለእምነታቸው ሲሉ የሰጡ ቅዱሳን ሰማዕታት ናቸው፡፡ እኛ በቃል ብቻ የምንናገረውን ሰማዕትነት በ21ኛው ክፍለ ዘመን በተግባር ያሳዩ የተግባር ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ምናልባት ባለ ሥልጣናቱና ሚዲያዎቹ ይህንን ለመናገር የከበዳቸው ሌሎች አማኞችን እናስከፋለን ብለው አስበው ይሆናል፡፡ እውነት ለመናገር ግን በግድ ሃይማኖታቸውን ወደ እስልምና (ያውም አይሲስ ወዳጣመመው የእስልምና አመለካከት) መቀየር ነበረባቸው ብሎ የሚከራከር ኢትዮጵያዊ ሙስሊም ይኖራል ብዬ አላምንም፡፡ ቢኖርም አመለካከቱን እንዲፈትሽ ማድረግ እንጂ እርሱን ላለማስቀየም እውነቱን መካድ አያስፈልግም፡፡ የአይሲስን ሐሳብ ተቀብለው፣ እምነቱን አራምደው፣ ከእርሱ ጋር ተቀላቅለው ለተወሰነም ጊዜ ቢሆን እድሜ ለማራዘም ቢፈልጉ መንገዱ ነበረ፡፡ ወላዋዮች፣ ለእምነት ግድ የለሾ፣ እምነታቸው እንደ ሸሚዝ ለመቀያየር የሚፈልጉ አቋም የለሾች ቢሆኑ ኖሮ ሞት ሩቅ ነበረ፡፡ እነ ኢያሱ፣ እነ ባልቻ፣ እነ ተስፋየና እነ ዳንኤል ግን እንደዚያ አልነበሩም፡፡ በእምነታቸው ጸኑ፤ በክርስቲያንነታቸው ታረዱ፣ ሰማዕትነትንም ተቀበሉ፡፡ይኼንን እውነታ መካድ ሰማዕታቱን ሁለት ጊዜ መግደል ነው፡፡ ከሞታቸው በላይ የሞቱበትን ክቡርና ቅዱስ ዓላማ መካድ አብልጦ ይገድላቸዋል፡፡ደግሞም ስደተኛነታቸው ለአደጋው ምክንያት ሆነ እንጂ የተሠዉት በስደተኛነታቸው አይደለም፡፡ ስደተኞችም ሆነው እምነታቸውን ለመለወጥ ቢፈልጉ ኖሮ ይችሉ ነበር፡፡ የተሠዉት በክርስትናቸው ነው፡፡ ክርስቲያን ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ አንገታቸውን የሰጡት ለክርስቶስ ነው፡፡ እንደ አግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳ አነጋገር ‹እንደ ንጹሕ መገበሪያ ስንዴ ሆነው› ለአምላካቸው ነው በመሥዋዕትነት የቀረቡት፡፡ እነርሱ አንገት የሰጡለትን ክርስትና እኛ ለመናገር ለምን ፈራነው?

(Click here for PDF)

በጎንደር ከተማ የሚገኙ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ የመንፈሳውያን ወጣቶች ማኅበራትና የማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማዕከል አባላት በላኩት መግለጫ በአሸባሪውና አረመኔው አይሲስ በኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ላይ የተፈጸመውን ጭካኔ አውግዘዋል፡፡ በመግለጫው ላይ እንደተገለጠው ‹‹‹‹ISIS›› የሽብር ቡድን 30 ኢትዮጵያውያንን ክርስቲያን በመሆናቸውና ሃይማኖታችንን አንቀይርም በማለታቸው ርህራሄ በጎደለው ሁኔታ አንገታቸውን በሰይፍ በመቅላትና በጥይት በመደብደብ የፈጸመው ዘግናኝ ተግባር ኢትዮጵያዊነትን የሚፈታተን፣ ታላቅ ኀዘንን በክርስቲያኖች ላይ ፈጥሯል፡፡›› ብሏል፡፡ በማያያዝም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው ሊደረጉ ይገባል ያሏቸውን አራት ሐሳቦች ለሀገረ ስብከቱ አቅርበዋል፡፡ የመግለጫውን ሙሉ ቃል ቀጥሎ መመልከት ይቻላል፡፡ ይህንን በመጫን መግለጫውን ያንብቡ


የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ባወጣው መግለጫ ከነገ ሚያዝያ 14 ቀን ጀምሮ ለሰባት ቀናት ጸሎተ ምሕላ ዐወጀ፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በአሸባሪዎች የተፈጸመውን ድርጊት አውግዞ ባወጣው ባለ ዘጠኝ ዐንቀጽ መግለጫ ለሰማዕታቱ ተገቢውን ቀኖናዊ ክብር እንደሚሰጥ ገልጧል፡፡ ለዚህም የሰማዕታቱን ቤተሰቦች የመረጃ ትብብር ጠይቋል፡፡ ‹‹የጀግና እናት አታለቅስም›› ያለው መግለጫው የሰማዕታቱ ቤተሰቦች የልጆቻቸው ሰማዕትነት በእግዚአብሔር ዘንድ ዋጋ ስላለው በዚህ እንዲጽናኑ አደራ ብሏል፡፡ ለወደፊቱ ተመሳሳይ ችግር እንዳይከሰት ከመንግሥት ጋር አብሮ የሚሠራ ዐቢይ ኮሚቴ እንደሚያቋቁምም ገልጧል፡፡
መግለጫውን ቀጥሎ ያንብቡት
በተያያዘ ዜና ዛሬ ከሰዓት ዐሥር ሰዓት ላይ በቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ወደ ሰማዕታቱ ቤተሰቦች በመሄድ ጸሎት እንደሚያደርጉና እንደሚያጽናኑ ተነግሯል፡፡  
ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲህ ሲሠራ ‹ሲኖዶስ ሲኖዶስ› ይላል፡፡

click here for pdf

ዛሬ እኩለ ቀን ላይ ከፖኤቲክ ጃዝ አባላትና ከሌሎች የኪነ ጥበብ ሰዎች ጋር ወደ ቂርቆስ ሄጄ ነበር፡፡ ያቺ ሳቂታዋና ተጫዋቿ ቂርቆስ ኀዘን ወርሯታል፡፡ የቂርቆስን ልጆች አውቃቸዋለሁ፡፡ ማልታ፣ ግሪክ፣ ጣልያን፣ ጀርመን፣ ፈረንሳይ፣ ስዊዘርላንድ አግኝቻቸዋለሁ፡፡ መሳቅ ነው፣ መጨዋት ነው፡፡ መቀለድ ነው፡፡ ችግር እነርሱ ጋር የለም፡፡ ካገኙ ተካፍለው ካጡ ተሳስቀው ያልፉታል፡፡ መተዛዘን፣ መረዳዳት፣ ነገር ማቅለል ማን ይችላቸዋል፡፡ እንግሊዝ ሀገር የደረሱት በመንገድ ያለቁትን የሚያስቡበት ዓመታዊ የመታሰቢያ ቀን አላቸው፡፡
ከቂርቆስ ልጅ ጋራ አብረው ቢሰደዱ
ቢያገኝም ያበላል ቢያጣም ያዝናል ሆዱ
ይላሉ የማልታ ልጆች፡፡

ዛሬ ያ ሁሉ ሳቅና ጨዋታ በኀዘን ተቀይሯል፡፡ የልጆቻቸውን መሞት በቪዲዮ በተመለከቱ ወላጆች፣ ማንነታቸውን ከቪዲዮው ለመለየት አቅቷቸው በሰቀቀን ውስጥ በሚገኙ ወላጆች፣ የልጆቻቸውን መረጃ ፈልገው መልስ ባጡ ወላጆች ቂርቆስ ተሞልታለች፡፡ ትጠይቃለች፤ መልስ ግን አላገኘችም፡፡ እንዴት ያለው ትምህርት፣ እንዴት ያለው ጥበብ፣ እንዴት ያለው ብልሃት እንደሚያጽናናት እንጃ፡፡  
እኔ በልቅሶ ቤት ሄጄ ብዙም አላለቅስም፡፡ ዛሬ ግን አለቀስኩ፡፡ በተለይ የባልቻ እናት ‹ፍቅር እስከ መቃብር› እያሉ ሲያለቅሱ ስሰማ ዕንባዬን መቆጣጠር አቃተኝ፡፡ ኢያሱና ባልቻ ሲበሉም፣ ሲጠጡም፣ ሲሄዱም፣ ሲቀመጡም የማይለያዩ አብሮ አደጎች ናቸው፡፡ ሲሰደዱም አብረው ነው የተሰደዱት፤ መሥዋዕት የሆኑትም አብረው ነው፡፡ ለዚህ ነው ‹ፍቅር እስከ መቃብር› የሚሉት የባልቻ እናት፡፡ እናቱን ሊረዳ እንደሄደ፣ ድሮም በእምነቱ ቀልድ እንደማያውቅ፣ ብዙ ተስፋ ሰጥቷቸው እንደነበረ እያነሡ ያለቅሳሉ፡፡ ‹‹እኔ ሲሞት እንዳላየው ብሎ አንገቱን ዘንበል አደረገ››  ይላሉ፡፡
 አያሌ የከተማው ሕዝብ ለእግር መቆሚያ እስኪጠብ ድረስ ሠፈሩን አጨናንቆታል፡፡ ኡኡታ፣ እሪታ፣ ሰቆቃ፣ ቁጭት፣ ሰቀቀን፣ ይነበባል፡፡ የባልቻ እናት ከልጃቸው ሞት በላይ አሁንም በሊቢያ የሚገኙ ሌሎች ወገኖቻችን ያሳስቧቸዋል፡፡ ስለ እነርሱም ያለቅሳሉ፣ ይወዘወዛሉ፡፡ አይ ኢትዮጵያዊት እናት፡፡  

በሊቢያ ምድር እምነታቸው ወንጀል ሆኖባቸው በአይሲስ የተሠዉትን ሰማዕታተ ሊቢያ በተመለከተ መንግሥታዊና የሃይማኖት ተቋማት ሊያደርጉ ስለሚገባው ነገር ስንለው ስንለው ቆየን፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ ወደ ባሕላችንና እምነታችን እንመለስ፡፡
እነዚህ ወገኖቻችን ስማቸውንና ቤተሰቦቻቸው ያሉበትን የምታውቁ ንገሩን፡፡ በባሕላችን መሠረት ልቅሶ እንድረሳቸው፡፡ ኀዘናቸው እነርሱ ብቻ አለመሆኑን እንንገራቸው፤ መከራቸውን እንካፈላቸው፡፡ እንደ ባሕሉ ማድረግ ያለብንን እናድርግ፡፡ ይኼ ከዘወትሩ ኀዘን ይለያል፡፡ የተሠዉበት ምክንያት፣ የተሠዉበት ሁኔታ፣ ለመሥዋዕትነት ያቀረቧቸው አሸባሪዎች ማንነት ከዘወትሩ ይለያቸዋል፡፡ ኀዘኑ የወላጅ፣ የዘመድ የመንደር፣ የዕድር ብቻ አይደለም፡፡ ከፕሬዚዳንቱ እስከ እኔ ላለነው ሁሉ ኀዘን ነው፡፡ ስለዚህም እንደየአመቺነቱ ከፕሬዚዳንቱ ጀምሮ በየደረጃው ያለን እንደ ኢትዮጵያዊነታችን ልቅሶ እንድረስ፤ ሰውነታችንን፣ ለዜጎቻችን ያለብንን ኃላፊነት፣ ለቤተሰቦቹ ያለንን የመጽናናት ምኞት በመግለጫ ብቻ ሳይሆን በባሕሉ መሠረት እንግለጠው፡፡ ፖለቲካዊ ዲስኩሩን፣ ነጥብ ለማስቆጠር መጨቃጨቁን፣ የተለመደ ቢሮክራሲያዊ አሠራሩን ትተን ወደ ባሕላችንና እምነታችን እንመለስ፡፡ ባሕል የሌለን እምነት የሌለን አንምሰል፡፡ ለእንደዚህ ያለ ወቅት የሚሆን ወግና ሥርዓት አለን፡፡  ያለ ወግ የመየጣውን ዕዳ በወግ እንክፈለው፡፡

ታዋቂ ሰዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የእምነት መሪዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሞያዎች፣ የሞያ ማኅበራት መሪዎች፣ ባለ ሀብቶች፣ በባሕሉ መሠረት ወደ ቤተሰቦቹ ሄደን ኀዘናችንን እንግለጥ፤ እንደ ኢትዮጵያዊ ኀዘናችንን እንካፈለው፡፡ ልዩነታችንን ኀዘን አንድ ሊያደርገው ካልቻለ ከእንግዲህ ምን አንድ ያደርገዋል፡፡
እንደ እምነታችን ለሰማዕታቱ ተገቢውን ሥፍራ እንስጥ፤ የጸሎት ሥነ ሥርዓት በየአጥቢያው ይዘጋጅ፤ ፎቶዎቻቸው በየአጥቢያው ይለጠፉ፤ የተሠዉበት ክቡር ዓላማ ይነገር፤ በየአጥቢያው የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ምዕዳን ነገሩን ያገናዘበ ይሁን፤ ቢቻል በየ ቤተ እምነቱ ልዩ መርሐ ግብር ይዘጋጅ፡፡ ስለ ሰማዕታቱ የሚያወሳ፣ሽብርና ሽብርተኛነትን የሚያወግዝ፣ ኢትዮጵያዊነትን የሚያጠነክር፤ በሐሳብ፣ በርእዮተ ዓለም፣ በአካሄድ ብንለያይም በሀገራዊ ጉዳይ አንድ መሆናችንን የሚያበሥር፣ የሰማዕታቱን ሰማያዊ ዋጋ የሚዘክር፤ ነገ ተመሳሳይ ነገር እንዳይደገም  መንገድ የሚቀይስ፣ ጉባኤ ይዘጋጅ፡፡
ይሄንን ነገር ያደረጉት አሸባሪዎች ናቸው፡፡ ይህንን ነገር ያደረጉት ኢሰብአውያን በመሆናቸው እንጂ ሙስሊም በመሆናቸው አይደለም፡፡ አንዱም ፍላጎታቸው እንዲህ ስሜት በሚነኩ ድርጊቶች ልዩነታችንን ማስፋት ነው፡፡ እኔ የብዙ ሙስሊም ወገኖቼን ስልክ ዛሬ ስቀበል ነበር፡፡ እጅግ ያዘኑ፣ የተነኩ፣ በእስልምና ስም በተፈጸመው ድርጊት ልባቸው የበገነ ሙስሊሞች፤ አማኞች እንጂ አሸባሪዎች ያልሆኑ፡፡ ሰው በእምነቱ የተነሣ መገደሉን በምንም መልኩ የማይቀበሉ ሙስሊሞች ኀዘናቸውን ሲገልጡ ነበር፡፡
ይኼንን ሰማዕታቱ የሰጡንን ዕድል ለአንድ ዓላማ ለመቆም እንጠቀምበት፤ የሰማዕታት ዓላማ ማስታረቅ ነው፤ ማግባባት ነው፡፡ ይኼንን የኢትዮጵያዊ መተዛዘንና መረዳዳት ጉዳይ ሙስሊም ወገኖቼ በእምነታቸውና በባሕላቸው አጉልተው ያሳዩናል ብዬ አምናለሁ፡፡ አንዳችን በሌላችን የኀዘን ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተን ከእኩዩ ተግባር በተቃራኒ በጋራ መቆማችንን እናሳይ፡፡  
ያ ከሆነ የደሙ ልቦች ይድናሉ፣ የተጎዱ ቤተሰቦች ከልብ ይጽናናሉ፤ አራጆቻችንም የፈለጉትን ማግኘት እንዳልቻሉ ያያሉ፡፡ አሸባሪዎቹ በሰማዕትነት እንዳከበሩን ሁሉ እኛ ደግሞ የሰማዕታቱን ዓላማ በማጽናት እናዋርዳቸዋለን፡፡ ማን ያውቃል፣ የሰማዕታቱ ደም አልግባባ ላለው ልዩነታችን ሥርየት ይሆነን ይሆናል፡፡

click here for pdf


የቅዱስ ሲኖዶሱን መግለጫ አየሁት፡፡ መጀመሪያ ነገር ቋሚ ሲኖዶሱ ተሰብስቦ መክሮበታል ብዬ ለማመን ይቸግረኛል፡፡ የተጻፈበት ቋንቋ ቤተ ክህነት ቤተ ክህነት አይልም፡፡ ለመሆኑ ለሰማዕታት የሚሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ አጥታችሁ ነው? ይበልጥ ያስገረመኝ ደግሞ የሰማዕታቱ ዜግነት ለቤተ ክርስቲያኒቱ ምን እንደሚጠቅማት ነው፡፡ መንግሥት የዜግነትን ጉዳይ ቢያነሣ ኃላፊነቱ በዜጎቹ ላይ የተወሰነ ስለሆነ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ግን ‹መልዕልተ ኩሉ› የተባለቺውን ዘንግታው ነው የዜግነት ጉዳይ ያሳሰባት? ምንም ኢትዮጵያዊነታቸው የማያጠራጥር ቢሆንም፣ ጠላታቸው እንኳን የመሰከረላቸው ቢሆንም፣ ዓለም ያወቃቸው ቢሆንም፣ ለቤተ ክርስቲያን ግን ሱዳኖችም ሆኑ ሩዋንዳዎች፣ ሶማልያዎችም ሆኑ ጅቡቲዎች የተሠውትኮ ክርስቲያኖች ናችሁ ተብለው ነው፡፡ ለአንድ ክርስቲያን የሰማዕትነት ክብሩ የሞተለት ክርስቲያናዊ ምክንያት ነው፡፡ የሞቱት ደግሞ ክርስቲያኖች ናችሁ ተብለው ነው፡፡ በቃ፡፡ 

ደግሞስ ‹የዜግነትና የማንነት መረጃውን በተመለከተ ግልጽ መረጃ ለማግኘት ጥረት እየተደረገ ነው› የሚሉን ማነው ጥረት እያደረገ ያለው? መንግሥት ነው ካላችሁ ‹መንግሥት ጥረት እያደረገ ነው› በሉ እናንተም ጥረት እያደረጋችሁ ከሆነ ንገሩን፡፡ ቤተሰቦቻቸውኮ ኢትዮጵያ ውስጥ ናቸው፡፡ ለምን ለየሀገረ ስብከቱ መመሪያ በመስጠት ቤተሰቦቻቸውን ለማግኘት ከበዳችሁ? እረኛ በጎቹን በሪሞት ይጠብቃል እንዴ?
እጅግ ያስገረመኝና ያሳዘነኝ ነገር ደግሞ ክርስቲያን በመሆናቸው በአሰቃቂ ሁኔታ ለተገደሉ ወንድሞች ከቤተ ክርስቲያን የምጠብቀውን ሦስት ነገር ከመግለጫው ማጣቴ ነው፡፡ የመጀመሪያው የመታሰቢያ ጸሎት ሊደረግ ይገባው ነበር፡፡ በምንም ለማናውቃቸውና ለማያውቁን የኢንዶኔዥያ ዜጎች ሱናሚ መታቸው ብለን በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ጸሎተ ፍትሐት ያደረግን ሰዎች ለሚያውቁንና ለምናውቃቸው ክርስቲያን ወገኖች ጸሎት ለማድረግ ለምን እንደከበደን እንጃ፡፡ ለመሆኑ ከአንድ አባት ከጸሎት በላይ ምን ሊገኝ ይገባ ነበር?
‹ማንነታቸው ተረድተን በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት አስፈላጊውን እናድርጋለን› ይላል መግለጫው፡፡ ለመሆኑ ከክርስትና በላይ ምን ማንነት አለ? የብሔር፣ የብሔረሰብ ማንነት ነው የምታጣሩት? ከዚያ ይልቅ ሁኔታውን የሚከታተል፣ ከቤተሰቦቻቸው ጋር የሚገናኝና ለቀጣዩ የቤተ ክርስቲያን ትውፊታዊም ቀኖናዊም ተግባር ነገሮችን የሚያመቻች ሲኖዶሳዊ ኮሚቴ ይቋቋማል ብዬ ጠብቄ ነበር፡፡ ምነው በአንድ አጥቢያ ገንዘብ ተወሰደ ሲባል ሲኖዶሳዊ ኮሚቴ ይቋቋም የለምን?
ሦስተኛው ያሳዘነኝ ነገር ቤተ ክርስቲያን በልጆቿ ላይ የሚደርሰውን ኀዘን የምትገልጥበት ቀኖናዊና ትውፊታዊ ሥነ ሥርዓት የሌላት ይመስል ኀዘንን በሴኩላር መንገድ ስትገልጥ ማየቴ ነው፡፡ እኔ የጠበቅኩት ለአንዳንድ ክርስቲያን ላልሆኑ ‹ታላላቅ ሰዎች› ቀብር እንኳን የሚከፈተው የቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተከፍቶ፣ ለቢዮንሴ እንኳን ያልተነፈጋት ማኅሌት ተቁሞ፣ በፓትርያርኩ የሚመራ ጳጳሳቱ የሚገኙበት የጸሎት ሥነ ሥርዓት ተደርጎ፣ መግለጫው በጸሎቱ ፍጻሜ ይሰጣል ብዬ ነበር፡፡ የመግለጫው አሰጣጥ ግን የዕለት ተዕለት ተግባርን በተመለከተ የሚሰጥ ሳምንታዊ መግለጫ ነበር የሚመስለው፡፡ ኦርቶዶክስ ኦርቶዶክስ አይሸትም፡፡ የተወካዮች  ምክር ቤት እንኳን የሦስት ቀን ብሔራዊ ኀዘን ሊያውጅ መሆኑን ሲገልጥ ቤተ ክርስቲያኒቱ ግን የጸሎት ሳምንት አለማወጇ የታሪክ ትዝብት ውስጥ የሚከታት ነው፡፡
እኔ የሲኖዶሱ መግለጫና አገላለጡ ወርዶብኛል፡፡ ሲኖዶሳዊም መስሎ አልታየኝም፡፡ ሊቃውንቱ ያዩት፣ ጳጳሳቱ የተወያዩበት፣ ቅዱሳት መጻሕፍቱ ያሹት፣ ቀኖናዎቹ የዳሰሱት፣ ትውፊቱ የነካው፣ ባሕሉ ያጠነው አልመስልህ አለኝ፡፡ ‹ወይ እንደ እስክንድ ተዋጋ ወይ የእስክንድርን ስም መልስ› አለ ታላቁ እስክንድር፡፡


የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሊቢያ በአሸባሪው አይሲስ እጅ በሰማዕትነት የተሠውትን ኢትዮጵያውያን በተመለከተ ዛሬ ጠዋት 5፡30 ላይ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ ብጹዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ከውጭ ሀገር ጉዞ ቀርተው በመንበረ ፓትርያርኩ የቅዱስ ሲኖዶሱን መግለጫ የሰጡ ሲሆን ሌሎች የእምነት ተቋማትም ተመሳሳይ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡
 መግለጫውን ተመልከቱት፡፡ 

በየመን፣ በደቡብ አፍሪካና በሊቢያ ስለሚሞቱት ዜጎቻችን የሚሰጡት መንግሥታዊ መግለጫዎች ሁለት ነገር የጎደላቸው ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ሰብአዊ ስሜት፡፡ ማንኛውም ሰብአዊ ፍጡር ስለሌላው ሰብአዊ ፍጡር መከራና ስቃይ ሲሰማ መጀመሪያ አንዳች የኀዘን ስሜት ይሰማዋል፡፡ ከዕውቀት ይልቅ ስሜት ለሰዎች ቅርብ ነውና፡፡ ባለሥልጣን ቢሆን፣ ፖሊስ ቢሆን፣ ዳኛ ቢሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሆን ሰው ነውና ስሜት አለው ተብሎ ይታሰባል፡፡ ያዝናል፣ ይከፋዋል፣ ልቡ ይረበሻል፣ ሆዱ ይባባል፣ ኅሊናው ይደማበታል ተብሎ ይታመናል፡፡ ስለዚህም የመጀመሪያው ሥራው ማዘን ቀጥሎም ኀዘኑን በወጉ መግለጥ ነው፡፡

ሰሞኑን የማያቸው መግለጫዎቻችን ግን የኀዘን ወግ በሀገራችን የሌለ የሚያስመስሉ ናቸው፡፡ መሪዎቻችን ወደ አደባባይ ወጥተው ለሞቱት ወገኖቻችን እንደ ኢትዮጵያዊነት ኀዘናቸው የሚገልጡት፣ ጥቁር ልብስ ለብሰው የምናያቸው፣ ነጠላ የሚያዘቀዝቁት ስንት ሰው ሲሞትብን ነው? የሚያስብሉ ናቸው፡፡ ኀዘንኮ ፖለቲካ አይደለም፣ ፓርቲ አይደለም፣ ርእዮተ ዓለም አይደለም፣ ሊብራልም አብዮታዊ ዲሞክራሲም አይደለም፡፡ ኀዘን ሰብአዊነት ነው፡፡ የሚመራቸው ዜጎቹ፣ የሚያሠማራቸው በጎቹ ሲታረዱና ሲሞቱ ኀዘኑን በይፋ የማይገልጥ መሪና እረኛ መቼ ነው ኀዘኑን የሚገልጠው?

ዜጎቹ በሕገ ወጥ መንገድም ይሂዱ በሕጋዊ፣ ድንበር ጥሰውም ይሂዱ በአውሮፕላን ተሳፍረው፤ መጀመሪያ ሰዎች፣ ቀጥሎም የዚህች ሀገር ዜጎች ናቸውና ኀዘን ይገባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ሰው አገኘዋለሁ ብሎ ከሚያስበው ክብር አንዱ በሞቱ ጊዜ የክብር ልቅሶና ኀዘን ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ከአካባቢያቸው ላለመራቅ፣ ከራቁም ለመመለስ ከሚሰጧቸው ምክንያቶች አንዱ ‹በክብር ዐርፎ በክብር መቀበርን፣ የክብር የኀዘን ሥነ ሥርዓትን ማግኘትን› ነው፡፡
ካገሬ እንዳወጣህ አገሬ መልሰኝ
በሹም የታዘዘ አፈር አታልብሰኝ፤
እንኳን የሚቀብረው የሚያዝንለት አጣ
ምን ወግ ማረግ ያያል ካገሩ የወጣ፤
የሚሉት ለዚህ ነበረ፡፡

የመንግሥት አካላት ለምን ይኼንን ለመዘንጋት እንደፈለጉ አልገባኝም፡፡ የደቡብ አፍሪካው ቃጠሎና ግድያ ሲመጣ የሀገራችን ፕሬዚዳንትና ጠቅላይ ሚኒስትር ብቅ ብለው ‹‹በወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ባለው ነገር ከልብ እናዝናለን፣ ከደቡብ አፍሪካ መንግሥት ጋር ተነጋግረን አስፈላጊውን እናደርጋለን፤ ተመሳሳይ ችግር ለወደፊቱ እንዳይከሰትም አንሠራለን› ዓይነት ሰውነት ያለበት መግለጫ ጠብቄ ነበር፡፡ የለም፡፡ ሲሆን በሀገራችን የልቅሶ ሥነ ሥርዓት መሠረት፡፡ አሁን ደግሞ ዓለም ያወቀው አሸባሪ ‹አይ ሲስ› ኢትዮጵያውያኑን በክርስትና እምነታቸው ብቻ ሲሠዋቸው የተሰጠው መግለጫ ስሜት የሌለበት፣ ማዘን መደሰታቸውን የማይገልጥ፣ እንኳን ሰው እንስሳ የሞተብን የማያስመስል ሆነ፡፡ ከማጣራቱም ከምኑም በፊትኮ ስሜቱ ይቀድማል፡፡፡ አዝናችኋል ወይ? ስትሰሙና ስታዩ ምን ተሰማችሁ? የአሜሪካ መንግሥት እንደዚያ ዓይነት መግለጫ ሲያወጣ ከኢትዮጵያ መንግሥት ያንን ነው ወይ መስማት ያለብን? ለመሆኑ መሪዎቻችን ኀዘናቸውን የሚገልጡት ምን ስንሆን ነው? ለምንድን ነው ሁሉም ነገር ፖለቲካ የሚሆነው?

ሁለተኛው የሚጎድለው ነገር ደግሞ ፍጥነት ነው፡፡ አትሌቶቻችን በኦሎምፒክ ሲያሸንፉ የባለሥልጣናቱ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት ሯጮቹ ቆርጠውት ካለፉት ሪቫን ቀጥሎ የሚመጣ ዜና ነበር፡፡ አትሌቶቹ ደክሟቸው ከመሬት ሳይነሡ የባለሥልጣናቱ መልእክት ለሚዲያ ይደርስ ነበር፡፡ በዚህ የሁላችንም ኀዘን በሆነው ጉዳይ ግን ለምን መዘግየት እንደተመረጠ ግልጽ አይደለም፡፡ ማጣረቱ፣ መረጃ መሰብሰቡ፣ ተጨማሪ የዲፕሎማሲ ሂደቶችን መሄዱ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ማዘን ግን ጊዜ አይወስድም፡፡ ቪዲዮው ተለቅቋል፡፡ ሲሞቱ እያየን ነው፡፡ መልካቸው የኛው ነው፡፡ አይሲስ የገደላቸው ‹ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች› ብሎ ነው፡፡ የዓለም ሚዲያዎች ያንኑ እያስተጋቡ ነው፡፡ ይኄ ለኀዘን ያንሳል? አፈፍ ብሎ ተነሥቶ ‹በሆነው ነገር እናዝናለን፤ ልባችን ተነክቷል፤ ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን እንመኛለን፤ ዝርዝሩን በየጊዜው እንነግራችኋለን› ለማለት ስንት ሰዓት ይወስዳል? የደቡብ አፍሪካው ችግር ደረሰ እንደተባለ ሙጋቤን ለውግዘት የቀደማቸው የለም፡፡ የኛዎቹስ የት ሄዱ?
መንፈሳዊ መሪዎችስ የት ናቸው? አንዳንዶቹ ውጭ ሀገር መሆናቸው እየተሰማ ነው፡፡ ሲሆን ይህንን ሲሰሙ አቋርጦ መምጣት፤ ካልሆነም ባሉበት ሆኖ አባታዊ ኀዘንን መግለጥና በእምነቱ የሚገባውን ማድረግ ይገባ ነበር፡፡ ሲኖዶሱስ ምን እየሠራ ነው? አልሰማም ይሆን? ዛሬ ጠዋት ቢያንስ በአዲስ አበባ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎት መደረግ አልነበረበትም? ባፈው ካይሮ ሄዳችሁ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ምንድን ነው ያያችሁት? በጎቹ እረኛ የላቸውም ማለት ነው? አባቶች የሚያዝኑት ምን ሲገጥማቸው ነው? እረኛው የሚያለቅሰው ስንት በጎች ሲታረዱ ነው?

ቤተ ክርስቲያኒቱ ነገሩን በዝምታ የምታልፈው ከሆነ እኛ እንደ ጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን ትውፊታዊ ቀኖና እነዚህን በክርስትናቸው ምክንያት የተሠው ክርስቲያኖች ‹ሰማዕታተ ሊቢያ› ልንላቸው ይገባል፡፡ የሰማዕትነታቸውንም በዓል ማክበር አለብን፡፡ በስንክሳሩ ማስገባት ባንችል ታሪካቸው በኅዳጉ ማስፈር አለብን፡፡ ማንም ይሁኑ ማን፣ በሚገባ የተማሩም ይሁኑ ያልተማሩ፣ ከመካከላቸው የማያምኑም እንኳን ቢኖሩ የተገደሉበት ምክንያት ክርስትና ነውና ሰማዕታት ናቸው፡፡ ያውም ‹ኢትዮጵያውያን ሰማዕታት›፡፡ በስንክሳሩ እንደምናነበው በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን የክርስቲያኖች መንደርና ቤተ ክርስቲያን እየተወረረ ክርስቲያኖቹ ሲሠው ገና ያልተጠመቁት፣ ነገሩ ያልገባቸው፣ ክርስትናን ለመቀበል ያልወሰኑት ሁሉ አብረው ተሠውተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ግን የተሠውበት ምክንያት ክርስትና በመሆኑ ሁሉንም ሰማዕታት ብላቸዋለች፡፡ የእነዚህም ክብር እንዲሁ ነው፡፡

እነርሱ በሰማይ ዋጋ አላቸው፡፡ አክሊለ ሰማዕታትንም ተቀብለዋል፡፡ እኛ ግን ሰማዕታቱን ባለማክበራችን ክብር ይጎድልብናል፡፡ ‹በረከታቸው ይደርብን› እንጂ ‹ነፍስ ይማር› አንልም፡፡

ዛሬ የዓለም መገናኛ ብዙኃን የ30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን በኢስላሚክ ስቴት በሰማዕትነት መገደል ሲዘግቡ ነበር፡፡ ሰው በእምነቱ ብቻ ሰማዕትነት የሚከፍልበት ዘመነ ሰማዕታት አንደገና ታድሶ እየተነሣ ነው፡፡ ትናንት ግብጻውያን ምእመናን የከፈሉትን ሰማዕትነት ዛሬ ኢትዮጵያውያኑ ከፍለውታል፡፡ ክርስቲያን መሆን ወንጀል ሆኖ፡፡ ሰማዕታቱስ ወደሚወዱት ጌታ ሄደዋል፡፡ ይህ ጊዜ ግን የኢትዮጵያ መንግሥትና የኢትዮጵያ የእምነት ተቋማት የሚፈተኑበት ጊዜ ነው፡፡ የግብጽ መንግሥትና የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ለግብጽ ሰማዕታት ያደረጉትን በቅርብ ዓይተናል፡፡ የኛዎቹ በሚዛን የሚመዘኑበት ወይ ቀልለው ወይም ከብደው የሚገኙበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ እግዚአብሔር ከሰማዕታቱ በረከት ይክፈለን፡፡

ባለፈው እሑድ፣ የትንሣኤ ዕለት ማልዳ ነው ከዕንቅልፏ የተነሣቺው፡፡ እናቷ ቤተ ክርስቲያን አድራ፣ አባቷ ደግሞ ሌሊት ከውጭ ሀገር ገብቶ ደክሟቸው እንደተኙ አልተነሡም፡፡ እርሷም በጠዋት የተነሣቺው ጓደኛዋ አደራ ስላለቻት ነው፡፡ ‹‹የቴሌቭዥን የትንሣኤ ፕሮግራም የተቀረጸው እኛ ቤት ነው›› ብላ አጓጉታታለቺ፡፡ የተነሣቺው ጓደኛዋን በቴሌቭዥን ለማየት ስትል ነው፡፡ ደግሞ ‹ዘፈን ምናምን አቅርቤያለሁ› ብላታለቺ፡፡ የጓደኛዋ አባት ‹ፍቅር እዚህም እዚያም›፣ ‹ትሄጅብኛለሽ› እና ‹ፍቅር በኪችን ውስጥ› የተሰኙ ሦስት አስቂኝ የፍቅር ፊልሞች ላይ የሠራ ‹ታዋቂ አርቲስት› ነው፡፡ ጓደኛዋ እንደነገረቻት ከሆነ የበዓሉ ፕሮግራም እነርሱ ቤት ሲቀረጽ የቀረ አርቲስት የለም፡፡ በዓሉ ራሱ ሕዝቡን ሊያዝናና ስለማይችል ‹ዘና እንዲያደርጉት› ተብሎ ቀልደኞቹ ሁሉ እነርሱ ቤት መጥተው ነበር፡፡ 

ከቀረፃው ማግሥት ጓደኛዋ ትምህርት ቤት ስትመጣ የታዋቂ አርቲስቶችን ፊርማ በየደብተሯ ሰብስባ መጥታ ጓደኞቿን ሁሉ ስታስቀናቸው ነበር፡፡ በርግጥ ክፍል ውስጥ እርሷና ጓደኞቿ ትምህርታቸውን ረስተው የአርቲስቶችን ፊርማ ሲያደንቁ ያዩዋቸው መምህራቸው እንደ መገሰጽ ቢያደርጉም፣ እንደመስማት ያላቸው ተማሪ ግን አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እርሳቸው ታዋቂ አይደሉማ፡፡ ደግሞ መምህር ከመቼ ወዲህ ነው ታዋቂ የሚሆነው፡፡ ይኼው ስንቱ አርብቶ አደርና አርሶ አደር ሲሸለም መምህር መቼ ተሸልሞ ያውቃል፡፡ በተለይ ደግሞ ብዙዎችን ተማሪዎች ያናደዳቸው ‹‹የዘፈነም፣ የተወነም፣ ፊልም የሠራም፣ ማስታወቂያ የሠራም አርቲስት አይባልም›› ያሉት ነገር ነው፡፡ ‹‹አርቲስት የሚለው ስም ለሰዓሊዎች የሚሰጥ ስም ነው፡፡  ያውም ስካልፕቸርና ፔይንቲንግ ለሚሠሩት ብቻ፡፡ እርሱም ቢሆን እንደ ደጃዝማችና ግራ አዝማች ማዕረግ ሳይሆን የሞያ መጠሪያ ነው፡፡ እስኪ አሁን አርቲስት ማይክል ጃክሰን፣ አርቲስት ቢዮንሴ ሲባል ሰምታችሁ ታውቃላችሁ? ሰው ማዕረግ የሚያበዛው ስሙ ብቻውን ለመቆም ዐቅም ስለሚያጣ ነው፡፡ እስኪ ተመልከቱ፡፡ ዳቪንቼ፣ ሼክስፒር፣ ሞዛርት፣ ፒካሶ የሚለው ስምኮ ብቻውን የሚቆም ነው፡፡ ዕዝል ቅጽል አያስፈልገውም፡፡›› ያሉትን ነገር ተማሪዎቻቸው ‹‹እርሳቸው ከቴሌቭዥን ሊበልጡ ነው እንዴ›› ብለው ሙድ ያዙባቸው፡፡
ለነገሩ እርሳቸውም አብዝተውታል፡፡ ‹አርሶ አደርና አርብቶ አደር፣ ሠልጣኝና የትራፊክ ፖሊስ፣ ታራሚና ፍርደኛ፣ ጋዜጠኛና ጎዳና ተዳዳሪ ማዕረግ ሆነው ከስም በፊት በሚቀጸሉባት ሀገር ‹አርቲስት› ማዕረግ አይደለም ብለው ተማሪን ማሸበር በአሸባሪነት የሚያስከስስ እንዳይሆን ያሰጋል፡፡ እንዲያውም ኢቲቪ ቢሰማቸው ‹በአሸባሪነት ሊያስከስስ ይገባል ሲሉ አንዳንድ የሕግ ምሁራን አስገነዘቡ› ብሎ ለዜና ጥብስ ያውላቸው ነበር፡፡
እርሷ ሶፋ ወንበር ላይ ተቀምጣ ይኼንን ሁሉ ስታስብ ጓደኛዋ በቴሌ ቭዥን ዘገየች፡፡ እስኪጀመር ድረስ ያቺ የ12 ዓመት የሰባተኛ ክፍል ተማሪ ማሰቧን ቀጠለች፡፡ ‹‹ቆይ ግን አባዬ ምንድን ነው? አንድም ቀንኮ በቴሌቭዥን ታይቶ አያውቅም፡፡ ይኼው ኤልዳና እንኳን ስንት ጊዜ በቲቪ ልትታዪ ነው፡፡ አባዬ ግን ዶክተር ምናምን ከሚሆን አርቲስት ቢሆን ነበር ጥሩ፡፡ እርሱ ዶክተር ሆኖ ምንም አልጠቀመንም፡፡ አንዴ አሜሪካ አንዴ ጃፓን፣ አንዴ ጀርመን ለወርክ ሾፕ መሮጥ ብቻ ነው፡፡ በርግጥ የኤልዳናም አባት ውጭ ይኼዳል፡፡ ግን እርሱ ሲሄድም ሲመጣም በሚዲያ ይነገርለታል፡፡ ሊሄድ ነው፣ እየሄደ ነው፣ ሊደርስ ነው፣ ደረሰ ይባልለታል፡፡ የኔን አባት መሄድና መምጣት ግን እኛና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ብቻ ነን የምናውቀው፡፡
ደግሞ የኤልዳና አባት ውጭ ሲሄድ ሰው ይከበዋል፣ ጉርድ ቀሚስ ያደረጉ ሴቶች፣ ቁጥርጥር የተሠሩ ወንዶች፣ አጅበውት ፎቶ ይነሣሉ፡፡ የኔ አባት ግን ፎቶዎቹን ሁሉ ሳይ ወይ ከራሰ በራ ሰው ጋር ወይ ድክምክም ካሉ ሴቶች ጋር ነው የሚነሣው፡፡ ደግሞኮ የኤልዳና አባት ሁልጊዜ የአበባ ጉንጉን ሲቀበል ነው የሚታየው፡፡ የኔ አባት ግን ሯጭ ይመስል ሜዳልያ ሲቀበል ነው የምናየው፡፡ ኤልዳና ቪዲዮውን በስልኳ ስታሳየን ሰው ሁሉ ኡኡ እያለ አዳራሽ ውስጥ ለአባቷ ይጨፍርለታል፡፡ የኔ አባት ግን አንድ ጠረጴዛ ነገር አጠገብ ይቆማል፤ የሆነ ነገር በፓወር ፖይንት ያሳያል፤ አንድ ጊዜ ይጨበጨብለታል፡፡ በቃ፡፡ አንድም የሚጨፍር ሰው አይታይም፡፡ አባዬ ግን ምንድን ነው?
ቆይ ግን እኛ ቤት ኢቲቪዎች የማይመጡት ለምንድን ነው? አባቴ አርቲስት ስላልሆነ ነው አይደል፡፡ የኔ አባትኮ እንኳን ለፋሲካ ለአርሂቡ ቀርቦ አያውቅም፡፡ እውነታቸው ነው፡፡ በአርሂቡኮ አርቲስቶች ሲቀርቡ ‹እንትናዬ አድናቂህ ነኝ፣ እወድሃለሁ፤ ቀጣዩ አልበምህ መቼ ነው የሚወጣው? ምን ፊልም ልትሠራልን ነው?›› የሚል ሰው ይደውልላቸዋል፡፡ አሁን አባዬ አርሂቡ ላይ ቢቀርብ ምን ሊባል ነው? ምን ተብሎ ሊጠየቅ ነው? ደግሞ ማንም አድናቂ አያገኝም፡፡ አልበም የለው፤ ፊልም የለው፣ ሰዎች በምን ያውቁታል፡፡
አባዬ ግን አርቲስት መሆን ነበረበት፡፡ ዶክተርነት ምን ያደርግለታል፡፡ አርቲስት ቢሆን ኖሮ በኋላ ሲያረጅ ‹የክብር ዶክትሬት› ተብሎ ይሰጠው ነበር፡፡ ‹የክብር አርቲስት› ብሎ ግን ማንም አሁን አይሰጠውም፡፡ ዶክተርነት ይደረስበታል፡፡ አርቲስትነት ግን አይደረስበትም፡፡ እንዲያውም እነርሱ ሲጠሩ ‹ክቡር ዶክተር› ነው የሚባሉት የኔ አባት ግን ‹ዶክተር› ብቻ ነው፡፡
እርሷ ይህንን ስታወጣና ስታወርድ የቴሌቭዥኑ ፕሮግራም ጀመረ፡፡ ጋዜጠኛውም ‹እያዝናናን እናስተምራለን› ብሎ የጓደኛዋን ቤት አሳየ፡፡ ምንም እንኳን የተቀረጸው በጾም ጊዜ ቢሆን ዶሮው፣ በጉ፣ ክትፎው፣ ቅቤው፣ ዕንቁላሉ ይታያል፡፡ ለነገሩ እንደ ኢቲቪ አቆጣጠር ጾሙ አንድ ሳምንት ሲቀረው ያልቃል፡፡ ከዚያ በኋላ ቀረጻ ይቻላል፡፡ ጓደኛዋን አየቻት፡፡ ቤታቸው እየታየ ነው፡፡
እየሮጠች አባቷን ቀሰቀሰቺው፡፡
‹‹ጓደኛዬ በቴሌቭዥን እየታየች ነው›› ስትለው ድካሙ ባይለቀውም እርሷን ለማስደሰት ተነሥቶ ዓይኑን እያሸ ወደ ሳሎን መጣ፡፡ ‹እያት ኤልዳናን› አለቺው፡፡ ኤልዳና እየተጠየቀቺ ነው፡፡ ቃለ መጠይቁ ሲያልቅ ‹አባዬ አንተ መቼ ነው በቲቪ የምትቀርበው› አለቺው ልጁ፡፡
‹‹ሚዲያችን ከታዋቂ ይልቅ ለዐዋቂ ቦታ ሲኖረው›› አላት አባቷ፡፡
‹‹አንተ ግን ለምን ታዋቂ አልሆንክም››
‹‹ልጄ እኔኮ ታዋቂ ነኝ፡፡ የኢቲቪ ጋዜጠኞች ግን አያውቁኝም፡፡ የቢቢሲ፣ የሲኤንኤን፣ የአልጀዚራ ጋዜጠኞች ያውቁኛል፡፡ እኔ አንድ ነገር ስለ ግብርና ከተናገርኩ ወይም ከጻፍኩ ያ ዜና ይሆናል፡፡ እዚህ አገር ግን ዕውቀት ዜና አይሆንም ልጄ፡፡ እዚህ ሀገር ዜና የሚሆነው ፖለቲካና ቀልድ ነው፡፡››
‹‹እሺ ለምን አርሂቡ ላይ አትቀርብም››
‹‹ያማ ጋዜጠኛውን ማሰቃየት ነው ልጄ››
‹‹ለምን ይሰቃያል?››
‹‹ምን ይጠይቀኛል? ጥናታዊ ጽሑፎቼን ማንበብ ሊኖርበት ነው፡፡ ምርምሮቼን መቃኘት ሊኖርበት ነው፡፡ ስለ እኔ የተሰጡ የሌሎች ሳይንቲስቶችን ምስክርነት ማገላበጥ ሊኖርበት ነው፡፡ ይሰቃያል ልጄ፡፡ ቀልድ የለመደን ሰው ዕውቀት ያሰቃየዋል፡፡በቀለላሉ የመጀመሪያ አልበምህ መቼ አወጣኸው? የመጀመሪያው ፊልምህ ምን ነበር? ገጠመኝህ ምንድን ነው? እያለ ሰዓቱን መሙላት ሲችል ምን በወጣው ሳይንቲስ አቅርቦ ይሰቃያል፡፡ ጋዜጠኞቹ መዘጋጀት ስለማይችሉም ስለማይፈልጉም አይደል እንዴ ‹እስኪ ራስሽን ለአድማጮች አስተዋውቂ› የሚሉሽ፡፡ ይኼኮ የጋዜጠኛው ሥራ ነበር፡፡ አንብቦ፣ ፕሮፋይል ሠርቶ ቢመጣ ኖሮ እንዲህ አይልም፡፡ ደግሞም አለቆቹም ላይወዱለት ይችላሉ፡፡ ዕውቀት የመለወጥ ኃይል አለው፡፡ ሕዝቡ ደግሞ እንዲዝናና እንጂ እንዲለወጥ አይፈለግም፡፡››
‹‹ተዪው እኔን፡፡ አንድ ገበሬ በዓል እንዴት ነው የሚያከብረው? ድንበር ላይ ባሉ ወታደሮች ዘንድ እንዴት ይከበራል? ተረኛ ሆነው ሆስፒታል ወይም እሳት አደጋ መከላከያ ውስጥ ባሉ ባለሞያዎች ዘንድ ፋሲካ ምን ዓይነት በዓል ነው? በዕለቱ አየር ላይ በሚሆኑ የአውሮፕላን አብራሪዎችና አስተናጋጆች፣ መርከብ ላይ በሚሠሩ ኢትዮጵያውያን፣ ሆስፒታል በተኙ ሕሙማን፣ በዓል እንዴት ይከበራል? የሚለውን እንኳን መች ያሳዩናል፡፡ ለምን ይመስልሻል?
‹‹እነርሱ ታድያ አርቲስት ናቸው እንዴ?››
››ልጄ የኑሮ አርቱማ ያለው እዚያ ውስጥ ነበር፡፡ የኛነታችንን ሌላ ገጽታ የምናየውማ እዚያ ውስጥ ነበር፡፡ ግን ይኼ ማሰብ ይጠይቃል፤ መመራመርን፣ ማንበብን፣ መዘጋጀትን ይጠይቃል፡፡ ማሰብ፣ ማንበብና መዘጋጀት ደግሞ እዚያ ቤት የሚወደዱ አይመስሉኝም››
‹‹እሺ ታድያ መቼ ነው የኛ ቤት በቴሌቭዥን የሚቀርበው?››
‹‹ወይ እኔ መቀለድ፣ ወይ እነርሱ ማወቅ ሲጀምሩ››
  

click here for pdf

በቤተ ክርስቲያን የጸሎት ሕይወት ውስጥ ታላቅ ቦታ ካላቸው ቅዱሳት መጻሕፍት አንዱ ‹መጽሐፈ ግብረ ሕማማት› ነው፡፡ ሊቃውንቱ ‹ግብር› የሚለውን ‹አገልግሎት› ብለው ይተረጉሙትና ‹ግብረ ሕማማት› ማለት ‹በሕማማት ወቅት የሚፈጸም አገልግሎት› ማለት ነው ይላሉ፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ‹እርሱ ሕመማችንን ተሸከመ›(ኢሳ 53÷4) በማለት የገለጠው ኃይለ ቃል ለሰሙኑም ሆነ ለመጽሐፉ ስያሜ መነሻ መሆኑንን ሊቃውንቱ ይገልጣሉ፡፡ ሐዋርያትም በሥርዓት መጽሐፋቸው ‹ወአንትሙሰ ተዐቀቡ ወግበሩ ተዝካረ ሕማማቲሁ – እናንተ ግን ተጠበቁ፣ የሕማማቱንም መታሰቢያ አድርጉ› ብለው ደንግገዋል (ግብረ ሕማማት፣ 1996፣9)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ‹ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማተ ወልዱ ክብረ ወስብሐተ – የልጁን ሕማማት ክብርና ምስጋና ብሎ የጠራ እግዚአብሔር ይመስገን› ብሎ ገልጦ ነበር፡፡ (ዝኒ ከማሁ፣10) 

ግብረ ሕማማት ከበዓለ ሆሳዕና እስከ በዓለ ፋሲካ የሚከናወነውን ሥርዓት የያዘ ትልቅ መጽሐፍ ነው፡፡ የመጽሐፉ የተወሰነ ክፍልና ሥርዓቱ ከ8ኛው መክዘ ቀደም ብሎ ጀምሮ በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ነበረ፡፡ አሁን ያለውን የግብጽ ቤተ ክርስቲያን የሰሙነ ሕማማት መጽሐፍ (ፓሻ) ያዘጋጁት አቡነ ገብርኤል 2ኛ(1131-1145) የተባሉት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ናቸው፡፡ ፓትርያርክ ገብርኤል አያሌ የመጽሐፍ ቅዱስና የሊቃውንት ትርጓሜ ዕውቀት ያላቸው ሊቃውንት በማሰባሰብ ለየሰዓቱና ለየኩነቱ የሚነበበውን ሥርዓትና ንባብ አዘጋጁ፡፡ ወደ ኢትዮጵያ የመጣው በሰላማ መተርጉም ጊዜ መሆኑን ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡(ዝኒ ከማሁ፣ 9) ከጎንደር መድኃኔዓለም ተወስዶ በብሪቲሽ ሙዝየም በሚገኘው ግብረ ሕማማት ላይ ከአባ ሕርያቆስ ድርሳን መጨረሻ ላይ ‹‹ዘንተ መጽሐፈ ዘተርጎመ ብፁዕ ወርቱዕ ሃይማኖት አቡነ አባ ሰላማ ይጽሕፍ ስሞ እግዚአብሔር ውስተ መጽሐፈ ሕይወት› ይላል፡፡ (catalogue Ethiopian manuscripts in British Library, 140) 
ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ እንደሚሉት ከሆነ ግብረ ሕማማትን አሁን ባለው መልክ ያዘጋጁት ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ናቸው፡፡ እስከ 14ኛው መክዘ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለሰሙነ ሕማማት የሚሆኑ የጸሎት ሥርዓት ሳይኖሯት ቆየች ማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ አቡነ ሰላማ መተርጉም የተወሰነውን የመጽሐፈ ግብረ ሕማማት ድርሳናት በመተርጎም ቀድሞ በነበረው የሰሙነ ሕማማት የጸሎት ሥርዓት ውስጥ መጨመራቸውን ይገልጣሉ፡፡ አሁን ባሉን የግብረ ሕማማት ቅጅዎች የአቡነ ሰላማን ስም የሚያነሣው ከሊቃውንቱ ደርሳናት መጨረሻ ላይ የሆነውም ለዚህ ሊሆን ይችላል፡፡ አቡነ ሰላማ መተርጉም ኢትዮጵያውያን ሊቃውንትን አሰባስበው የትርጉም ሥራ ይሠሩ የነበሩት በደቡብ ጎንደር ስማዳ በምትገኘው ደብረ ዕንቁ ማርያም ነበር፡፡ አቡነ ሰላማ የግብጹን ግብረ ሕማማት ይዘውት የመጡ ይመስላል፡፡ በደብረ ዕንቁ የነበሩ ሊቃውንት መጽሐፉን መነሻ በማድረግና ከቀደመው የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ጋር በማስማት አሁን የምናውቀውን ግብረ ሕማማት አዘጋጅተውልናል፡፡ 
እስካሁን ባሉን መረጃዎች ረጅም እድሜ ያስቆጠሩት የግብረ ሕማማት ቅጅዎች በ15ኛው መክዘ የተጻፉት ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል ሦስቱ በኢትዮጵያ ማይክሮ ፊልም ቤተ መጻሕፍት ውስጥ ይገኛሉ፡፡ (EMML 1765, 4434, 4752) EMML 1765 የሐይቅ እስጢፋኖስ ቅጅ ሲሆን በዚህ መጽሐፍ ላይ ልዩ ልዩ ድርሳናትን የተረጎሙት አባ ሰላማ መሆናቸውን ይገልጣል፡፡ EMML 4434 የእንዳፍሬ ማርያም(ሞረት) ሲሆን EMML 4752 ደግሞ ሰሜን ሸዋ የሚገኘው የሙሽ ዜና ማርቆስ ንብረት ነው፡፡
በግብረ ሕማማት ውስጥ ከጾመ ድጓና ምዕራፍ የተወሰዱ ጸሎቶች መኖራቸው፤ በግብጹ መጽሐፍ ላይ የሌሉ ከተአምረ ማርያምና ክተአምረ ኢየሱስ የሚነበቡ ምንባባት መገኘታቸው፤ እንዲሁም የቀረቡት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በቅርጽ ካልሆነ በቀር በብዛትና በዓይነት የተለዩ መሆናቸው ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የመጽሐፉን መነሻ ከግብጽ ወስደው ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንዲሆን አድርገው ማዘጋጀታቸውን እንደሚያሳይ የሚገልጡ አሉ፡፡ ለብዙ ዘመናት ግብረ ሕማማት በግእዝ ብቻ የሚገኝ መጽሐፍ ነበር፡፡ በ1990(?)ዓም በሊቀ መዘምራን ላዕከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ(ዘአሰላ) ወደ አማርኛ ተተርጉሞ በትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ታትሟል፡፡
በግብረ ሕማማት ውስጥ ሦስት ነገሮች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ጸሎት ሲሆን ‹ዐማኑኤል አምላኪየ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም› እየተባለ የሚጸለየውና ካህናትና ምእመናን በየመካከሉ የሚደግሙት ዳዊት የዚሁ መገለጫ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ስግደት ነው፡፡ በመጀመሪያው ሰዓት፣ በሦስት፣ በስድስት፣ በዘጠኝና በ11 ሰዓት ከጸሎት ጋር የሚደረግ ስግደት አለ፡፡ በዕለተ ዓርብ ደግሞ የ12 ሰዓት ጸሎትና ስግደት አለው፡፡ ከግብረ ሕማማት ትልቁን ቦታ የሚይዘው ሦስተኛው ክፍል ንባቡ ነው፡፡
በሰሙነ ሕማማት በመጽሐፈ ግብረ ሕማማት መሠረት የሚነበቡ ብዙ ምንባባት አሉ፡፡ እነዚህንም በአራት መድበን መመልከት እንችላለን፡፡
1.      መጽሐፍ ቅዱስ፡- በተለይም በዋናነት ከብሉይ ኪዳን ከኦሪት፣ ከጥበብ መጻሕፍት(ምሳሌ፣ መኃያ መኃይ፣ ጥበበ ሰሎሞን፣ ሲራክ፣ ኢዮብ)፣ ከመጽሐፈ ኢያሱ፣ ከመጽሐፈ ሩትና ከሌሎችም የሚቀርቡ ከሰሞኑ ጋር የሚሄዱ ምንባባት አሉ፡፡
2.     ትርጓሜ፡- የልዩ ልዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ትርጓሜ ይነበባል፡፡ በተለይ ደግሞ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዕብራውያን ትርጓሜ ትልቅ ቦታ አለው፡፡ ከእርሱም ጋር የኤጲፋንዮስ፣ የአትናቴዎስ፣ የቄርሎስና የያዕቆብ ዘሥሩግ ትርጓሜያት ይሰማሉ፡፡
3.     ምዕዳን፡- በግብረ ሕማማት የክርስቲያንን ልዩ እሴቶች የሚመለከቱ ምክሮች ይቀርባሉ፡፡ ስለ ፍቅር፣ ይቅርታ፣ ወገንን መርዳት የተመለከቱ ምንባባት አሉ፡፡
4.     መጻሕፍተ ሊቃውንት፡- በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከተዘጋጁና እምብዛም ከማናገኛቸው ድርሳናት መካከል በግብረ ሕማማት ውስጥ የምንሰማቸው አሉ፡፡ መጽሐፈ ዶርሖ፣ ላሃ ማርያም ለዚህ ማሳያ ናቸው፡፡ ከተለመዱት ምንባባት ደግሞ ስንክሳር፣ ተአምረ ኢየሱስና ተአምረ ማርያም ይጠቀሳሉ፡፡
   በተለይ በአሁኑ ጊዜ መጽሐፉ በአማርኛ የሚነበብ በመሆኑ ምእመናን ሁላችን በማስተዋል ብናዳምጥ በሌላ ጊዜ የማናገኛቸውን የቤተ ክርስቲያን ታሪኮች፣ ምሥጢራትና ምንባባትን የምናዳምጥበት ዕድል ይሆናል፡፡ የኛን ግብረ ሕማማት ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጋር ለማነጻጸር ይኼን መሥመር በመከተል የእነርሱን ግብረ ሕማማት በእንግሊዝኛ መመልከት ይችላል፡፡ http://ixoyc.net/data/Fathers/118.pdf
መልካም ሰሙነ ሕማማት፡፡

በግእዝ የተጻፉ ጥንታውያን መዛግብት ከተጻፉበት ዓላማ በተጨማሪ ሌሎችንም አገልግሎቶች ሲሰጡ ኖረዋል፡፡ አብዛኞቹ የተጻፉት ለሃይማኖት ማስተማሪያነትና ለታሪክ መመዝገቢያነት ቢሆንም በየዘመናቱ የተፈጠሩትን ማኅበራዊ ክስተቶች ተከትለው ሌሎችንም አገልግሎቶች ሰጥተዋል፡፡
በዚህ ጥናታዊ ጽሑፍ አንደኛውን እንመለከታለን፡፡ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍት እንደ ሰነዶች  ምዝገባና ማረጋገጫ ጽ/ቤት ሆነው ሲያገለግሉ የኖሩበትን አሠራር፡፡
በጥንታውያን የግእዝ የብራና  ጽሑፎች  ላይ ከሃይማኖታዊና ታሪካዊ ይዘቶች በተጨማሪ በመጻሕፍቱ መጀመሪያና መጨረሻ በሚኖሩ ባዶ የብራና ቅጠሎች፣ በኅዳጎች፣ በራስጌና  በግርጌ ክፍት ቦታዎች ላይ ውሎችን፣ ቃል ኪዳኖችንና ስጦታዎችን ሲመዘግቡ ኖረዋል፡፡ እነዚህ ምዝገባዎች በተዋዋዮቹ፣ በገዥዎቹና  ሻጮቹ፣  በስጦታ ሰጭዎቹ ወዘተ መካከል የሚኖሩትን ስምምነቶች በማስፈር እንደ ሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ ጽ/ቤት እየሆኑ ማገልገላቸውን ያሳዩናል፡፡
( ጥናታዊ ጽሑፉን ቀጥሎ ካለው የፒዲኤፍ ፋይል ይመልከቱ)


የጉዞው መሥራቾች

ትናንት(እሑድ መጋቢት 13 ቀን 2007 ዓም) በጨጨሆ የባሕል ምግብ አዳራሽ በተደረገ አንድ መርሐ ግብር ተጋብዤ ተገኝቼ ነበር፡፡ ‹ጉዞ አድዋ› ይባላል መርሐ ግብሩ፡፡
 ከዛሬ 119 ዓመት በፊት ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችን በዓለም ታሪክ ያልተለመደ አዲስ ታሪክ ለመሥራትና ኢትዮጵያ የምትባለውን ሀገር የማይደረስበት ከፍታ ላይ ለማስቀመጥ ሲሉ ከመላዋ ሀገሪቱ አንድ ሆነው ወጥተው፣ አንድ ሆነው ወደ አድዋ ዘምተው ነበር፡፡ ያኔ ብዙዎቹ የተጓዙት በእግራቸው ጋራ ሸንተረሩን፣ አረሁን ገደሉን እየተሻገሩ በፍጹም ኢትዮጵያዊ ወኔና ሀገራዊ ፍቅር ነበር፡፡ ያ አንድነትና የሀገር ፍቅር ስሜት ነበር ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችንን ሊደግሙት እንጂ ሊረሱት የማይገባ ታሪክ እንዲሠሩ ያደረጋቸው፡፡

ይህንን የአድዋ መንፈስና ዝና፣ ክብርና ላቅ ያለ ኢትዮጵያዊነት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ፤ አድዋ እንደ አንድ ተራ ሥነ ሥርዓት በምኒልክ አደባባይ የአበባ ጉንጉን ከማስቀመጥና ‹አስቦ ከመዋል› የዘለለ ትውልዳዊ ፋይዳ እንዲኖረው ለማድረግ፤ አድዋ እንደ ባለሞያ ጠጅ በየጊዜው ከጥንስሱ እየተቆነጠረ በየትውልዱ እንዲጠጣ ለማስቻል፤ እንደ ሰራፕታ ዱቄት በየዘመናቱ ቡኾ ውስጥ እንደ እርሾ እየተጨመረ እንዲበላ ለማብቃት፣ አድዋ ላይ የታየው የላቀ ኢትዮጵያዊነት አንደ ሜሮን ቅብዐት ከትውልድ ትውልድ ሳይቋረጥ እየፈላ የሁሉ ማጥመቂያ እንዲሆን የተነሡ ወጣቶች ያዘጋጁት መርሐ ግብር ነበር፡፡ እንደ አድዋ ዘማቾች ወኔ እንጂ ሌላ ሀብት የሌላቸው ወጣቶች፡፡ 
እነዚህ ወጣቶች አንድ አስደማሚ ተግባር ጀምረዋል፡፡ በየዓመቱ የአድዋ በዓል ከመከበሩ ቀደም ብለው ከአዲስ አበባ በመነሣት በእግራቸው ወደ አድዋ መዝመት፡፡ አባቶቻቸውና እናቶቻቸው በእግራቸው የተጓዙትን መንገድ እነርሱም በእግራቸው መከተል፡፡ የቀድሞ የአድዋ ዘማቾችን ስሜት  እየተጋሩ፣ ታሪካቸውን እያጠኑ፣ በየደረሱበት ለሚያገኙት ሁሉ የአድዋን የላቀ ኢትዮጵያዊነት እየሰበኩ፣ የትውልድን ቃል ኪዳን ማደስ፡፡

ተጓዦቹ ከመልስ በኋላ

በድንኳን እያደሩ፣ ያገኙትን እየቀመሱ፣ ከአራዊት ጋር እየታገሉ፣ ከተራራና ገደል ጋር እየተገዳደሩ፣ እየወደቁ እየተነሡ፣ እየታመሙ እየተፈወሱ፣ እየደከሙ እየጀገኑ፣ እያዘገሙ እየፈጠኑ ከአንድ ሺ ኪሎ ሜትር በላይ የሚሆነውን መንገድ በእግር ማቆራረጥ፡፡ አድዋ ላይ ተጉዘው የታሪክ ማርሽ በዘወሩ ጀግኖች ስም ራሳቸው እየሰየሙ፣ የመንፈስ ወራሽታቸን ማረጋገጥ፡፡  
የዘንድሮ ተጓዦች ስድስት ናቸው፡፡ ከስድስቱ አንዷ ሴት ናት፡፡ ጽዮን ትባላለች፡፡ በጉዞው ስሟ ደግሞ እቴጌ ጣይቱ፡፡ ከአንድ ሺ ኪሎ ሜትር በላይ የሚሆነውን መንገድ በእግሯ አቆራርጣ እንደ እቴጌ ጣይቱ አድዋ ላይ ሰንደቋን ተክላለች፡፡ መድረኩ ላይ ወጥታ የእቴጌን ታሪክና የጉዞውን ትዝታ ስትተርክ የሆነ የሚንፎለፎል ትኩስ ወኔ ከውስጧ እየወጣ ይገርፈን ነበር፡፡ እናለቅሳለንም፣ እንገረማለንም፣ እናጨበጭባለንም፡፡ የማትነጥፍ ሀገር፡፡
ከጉዞ አስተባባሪዎች አንዱ የሆነው መሐመድ ስለ ጉዞው ዓላማና ሂደት ሲገልጥ እርሱ ራሱ ከዐፄ ምኒሊክ ሠራዊት ጋር የዘመተ ነበር የሚመስለው፡፡ መቼም መሐመድ ስለ ኢትዮጵያ ሲያወራ መስማት በባለሞያ ካህን የተከሸነ ቅዳሴ እንደመስማት ያለ ነው፡፡ ያወጣዋል፣ ይተርከዋል፣ ያውም ከዕንባና ከስሜት ጋራ፡፡
እነዚህ ወጣቶች የዛሬ ዓመት በ2008 ዓም አንድ ታላቅ ታሪክ ሊሠሩ አስበዋል፡፡ የአድዋ አንድ መቶ ሃያኛ ዓመት ሲከበር አንድ መቶ ሃያ ተጓዦችን ይዞ ወደ አድዋ በእግር ለመዝመት፡፡ ወጣቶች ናቸው፡፡ ግን ልባቸው ሸምግሏል፤ ብዙ ሊስቧቸው የሚችሉ  ብልጭልጭ ነገሮች ነበሩ፤ ነገር ግን ሀገራዊውን ታሪክ መርጠዋል፡፡ ከሺ ኪሎ ሜትር በላይ የሚሆነውን መንገድ በእግር አቆራርጠው፣ የሀገራችንን ባንዴራ ከፍ አድርገው ፣ በየደረሱበት አድዋ ላይ የተገለጠውን ያንን ሁላችንንም የሚያኮራ ኢትዮጵያዊነት እየተረኩ በእግራቸው ሊጓዙ ተነሥተዋል፡፡

ጽዮን – እንደ እቴጌ ጣይቱ

እንደ እኔ እንደ እኔ አንድ ትውልድ ታሪኩን ሲያነሣ፣ በማንነቱ ሲኮራ፣ ታሪክም ለመሥራት ሲቆርጥ መደገፍ ይገባል እላለሁ፡፡ ወጣቶች ከሥነ ምግባር ሲወጡ፣ ማንነታቸውንና ታሪካቸው ሲረሱ፣ ለሀገራዊ ነገሮችም የእኔነት ስሜት ሲያጡ እንደምንወቅሰውና እንደምናዝነው ሁሉ፤ በሀገር ፍቅር ስሜት ሲነሡና ታሪካችንን ከፍ አድርገው በአዲሱ ትውልድ አዲስ መንፈስ ውስጥ ሊጽፉት ሲተጉም አብረናቸው መሥራት ይገባናል፡፡ ታሪካችንና ማንነታችን እንደማይዘነጋ ማረጋገጥ የምንችለው ተተኪው ትውልድ የእኔ ነው ብሎ በራሱ መንገድ ሊገልጠው ሲሞክር ካየን ብቻ ነው፡፡

የጉዞው አስተባባሪ ያሬድ ሹመቴ

እናግዛቸው፣ አብረናቸውም እንቁም፤ የቻልን የጉዟቸውን ወጭ እንጋራ፣ ያልቻልን በሚደርሱበት ቦታ ሽሮ ሠርተን ውኃ ቀድተን በማስተናገድ የጥንት አያቶቻችን የአድዋ ዘማቾችን የሸኙበትን ታሪክ እንድገመው፡፡ በሚደርሱባቸው ቦታዎች ያሉ ትምህርት ቤቶች ደግሞ ወጣቶቹ ከተጓዦቹ  ጋር ስለ ታሪካቸው እንዲወያዩ መርሐ ግብር ያዘጋጁ፡፡ የእምነት ተቋማት ደግሞ በሚደርሱባቸው ቦታዎች በመቀበል ለታሪካችንና ማንነታችን ያለንን የከበሬታ ሥፍራ እናሳይ፡፡ በየቦታው የምንገኝ ኢትዮጵያውያንም በየደረሱበት ቦታ እየተቀበልን ባንዴራውን ከፍ አድርገን በማሻገር የታሪክ ተረካቢነታችን እናረጋግጥ፡፡ አንድ መቶ ሃያኛውን የአድዋ በዓል፣ በ2008 ዓም ከአበባ ማኖር በዘለለ በማይረሳ የወጣቶች ታሪካዊ ጉዞ እናክብረው፡፡  
ጠቢብ አስቦ ይሠራል
ጎበዝ ደግሞ ከሚሠሩት ጋር ያብራል፡፡     

የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ተቋምን አሠራር በተመለከተ ለተዘጋጀው ጉባኤ የቀረበ
 ባሕር ዳር
 የካቲት 3-5 ቀን 2007 ዓም


የአማርኛ ቋንቋ ታሪካዊ ጉዞ
የአማርኛ ቋንቋን ጉዞ በአጭሩ ለመመልከት እንድንችል፣ የዚህን ታላቅ ጉባኤ ጊዜንም ላለመውሰድ በአምስት ምዕራፍ ማየቱ ይጠቅማል ባይ ነኝ፡፡ እነርሱም
1.    ከጥንት እስከ 13ኛው መክዘ
2.   ከ13ኛው መክዘ እስከ 16ኛው መክዘ
3.   ከ16ኛው መክዘ እስከ ዘመነ ቴዎድሮስ
4.   ከዘመነ ቴዎድሮስ ዘመነ ምኒሊክ
5.   ከዘመነ ምኒሊክ እስከ አሁን

 

 1.   ከጥንት እስከ 13ኛው መክዘ
አማርኛ በዚህ ዘመን እንዲህ በሚባል ሕዝብ መነገር ጀመረ ብሎ ለማስቀመጥ አስቸጋሪ መሆኑን ያጠኑት ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡ አገኛኘቱን በተመለከተ እስካሁን ቦታ ይዘው የሚከራከሩ ሁለት ዓይነት አመለካከቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው፣ በሰፊው የሚነገረውና ለብዙ ዓመታት የቆየው አመለካከት አማርኛ ከሌሎች ቋንቋዎች ተቀይጦ ምናልባት በ4ኛው መክዘ አካባቢ ከአኩስም ወደ ደቡብ በመጡ ዘማቾችና አዝማቾች አማካኝነት የተፈጠረ(pidgin theory) ነው የሚል ሲሆን በዚህ መላ ምት መሠረት ከሰሜን ወደ ደቡብ እየተስፋፋ የመጣ፤ ከግእዝ ትንሽ ለየት ያለ ሴማዊ ቋንቋ በሚናገሩ አዝማቾችና የኩሽ፣ የኦሞና የዓባያዊ ቋንቋዎች በሚናገር ዘማች ሠራዊት አማካኝነት የተፈጠረ ነው፡፡
 አዝማችና ዘማች በአገዎች ምድር ሲቀመጡ ልዩ ልዩ ቋንቋ ይናገር የነበረው ዘማች የአዝማቾቹን ሴማዊ ቋንቋ መናገር ይጀምራል፡፡ ሲናገር ግን ከራሱ ቋንቋ ጋር እያስማማ ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ የሴማዊ ቃላትን ከራሱ ቃላት እያመሳሰለና እያዳቀለ ይናገር ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ የቃላቱ ቅርጽና የመዋቅሩ ሥርዓት ቀስ በቀስ እየተለወጠ መጣ፡፡ ሴማዊ ጠባዩን እየተወም ‹ኩሾ ኦማዊ› እየመሰለ መጣ፡፡ እየቆየም ራሱን የቻለ ቋንቋ ሆኖ በስፋት በሚነገርበት አካባቢ ስም ‹አማርኛ› ተባለ የሚለው ነው፡፡
የዚህን መላ ምት ዝርዝር የፈለገ የባየ ይማምን(2000) እና የቤንደርን(1983) ማንበብ ይጠቅመዋል፡፡
ሁለተኛው መላ ምት ከመጀመሪያው ጋር ሲነጻጸር  የቅርብ ዘመን ሲሆን አማርኛ ከአማርኛ በፊት ከነበረ የአርጎባ – አማርኛ እናት ቋንቋ በተለምዶ ከሚታወቅበት የጥንቱ አምሐራ አካባቢ በስተ ደቡብ የተገኘ ቋንቋ ነው የሚል ነው(proto Amharic- argoba, theory)፡፡ በዚህ መላ ምት መሠረት ስሙን በትክክል ዛሬ ለመጥራት ባንችልም ራሱን የቻለ አማርኛን የሚናገር ሕዝብ ነበረ፡፡ ይህ መላ ምት በኢትዮጵያ ታሪክ የተለመደ ትርክት የምንሰማውን የኢትዮ ሴማውያን ቋንቋ ተናጋሪዎችን የሰሜን – ደቡብ የፍልሰት አቅጣጫ በመቀየር ከደቡብ ወደ ሰሜን የሚያደርግ ነው፡፡ ለዚህም ዋና መከራከሪያው አብዛኞቹ የኢትዮ ሴማውያን ቋንቋ ቤተሰቦች የሚገኙት በደቡቡ ክፍል በመሆናቸው፣ ‹የሚሰደደው ጥቂቱ ነው› በሚለው መሠረተ ሐሳብ መሠረት የኢትዮ ሴማዊ ቋንቋዎች ከደቡብ ወደ ሰሜን የፈለሱ ናቸው ይላል፡፡ የአማርኛ እናት ቋንቋና ራሱ አማርኛም ኦሮምኛ በ16ኛው መክዘ እንዳደረገው ከደቡብ ወደ ሰሜን የተጓዘ ቋንቋ ነው ይላል፡፡ ይህንን መላ ምት በሚገባ ለማወቅ የግርማ አውግቸውን መጽሐፍ (The Origin of Amharic, 2009) እና የአየለ በከሪን (1997) መጻሕፍት መመልከቱ ይጠቅማል፡፡
እስከ 13ኛው መክዘ ያለው የአማርኛ ቋንቋ ታሪክ በሚገባ ሊታወቅ አልቻለም፡፡ በቂ መረጃዎችም አልተገኙም፡፡ በተለይ ከአርጎባ፣ ከሐረሪና ከዛይ ቋንቋዎች ጋር በጋራ የሚደረጉ የሥነ ልሳን ጥናቶች፣ ከዚህም ባሻገር ብዙ ጠባያቱን ከሚጋሩት የኩሽና የኦሞ ቋንቋዎች ጋር በማነጻጸር ቢጠና ዕውቀታችን ከዚህ የተሻለ ሊሆን የሚችልበት ዕድል አለው(ባየ፣ 2000፣ xviii & xix):: የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ተቋምን የሚጠብቀው አንዱ ሥራም ይኼው ይመስለኛል፡፡
2.    ከ13ኛው እስከ 16ኛው መክዘ
ይህ ዘመን ከአማርኛ ቋንቋ ቀደምት ዘመናት መካከል የተሻሉ መረጃዎች የተገኙበት ዘመን ነው፡፡ በአንድ በኩል አማርኛ  በዛጉዌና እንደ ገና በመጣው ‹ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት› ውስጥ ልሳነ መንግሥት ሆኖ የወጣበት( ባየ፣ 2000፣ xvii-xviiiGirma, 2009,210) ሲሆን በሌላ በኩልም በዋናነት ይነገርበት የነበረው አካባቢና የሚነገርበት ደረጃም  በውል ተለይቶ መታወቅ የጀመረበት ዘመንም ነው፡፡ የዛግዌ ነገሥታት የአኩስም መንግሥት ጠንካራ መሠረት ከሆነው የዛሬው ኤርትራና ትግራይ አካባቢ ይልቅ ደቡቡን በመጠቀም ጠንካራ አጋርና መሠረት ለማግኘት ባደረገው ጥረት አማርኛ ተናጋሪዎቹ የመንግሥቱን ቦታ እያገኙ ሲመጡ አማርኛም ልሳነ ንጉሥ መሆን ጀመረ፡፡ ይህም በንጉሥ ላሊበላ ዘመን መሆኑ ይታመናል (Sergew,1972,278):: በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ ነገሥታት ( ከሸዋ ወደ ጎንደር ከመጣው ከሠርፀ ድንግል በቀር፣) አዳዲስ ሥርወ መንግሥት ሲመሠርቱ ከሰሜኑ እየራቁ ወደ ደቡብ ነው የሚመጡት፡፡ ዛግዌ ላስታን ይዞ ወሎን በጌምድርና ጎጃምን፣ ይኩኖ አምላክ ሸዋን ይዞ ዳሞትን፣ ምኒሊክ ሸዋን ይዞ ደቡብ፣ ምዕራብና ምሥራቅን ነው ደጀን ያደረጉት፡፡ ይኼም የቀድሞው ሥርወ መንግሥት ከነበረው ጠንካራ መሠረት ለቅቆ ሌላ ጠንካራ መሠረት ለመፍጠር ነው፡፡  
በዐፄ ይኩኖ አምላክ ጊዜ በጥበበ እድ ሥራቸው የበለጸጉትን የጋፋት ሕዝቦችን ድጋፍ አግኝቶ የዛግዌን ነገሥታት ድል ሲነሣና ከዛግዌ ነገሥታት ዋና መሠረት ላስታ መንግሥቱን የጋፋቶች ዋና ቦታ ወደ ሆነው ሸዋ ሲያዛውር ለአማርኛ የበለጠ ዕድል ተፈጠረለት፡፡ ቋንቋውም ይበልጥ ከኦሞ ኩሽቲክ ቋንቋዎች ጋር ለመገናኘትና ለመወራረስ በቃ፡፡
ምንም እንኳን አማርኛ የግእዝን የሥነ ጽሑፍና የትምህርት ቋንቋነት ባይረከብም፤ የቤተ መንግሥቱ የፕሮቶኮል ቋንቋ ባይሆንም የዐፄ ዓምደ ጽዮን(1314-1344)፣ የዐፄ ዳዊት(1375-1404)፣ የዐፄ ይስሐቅ(1413-1430)፣ የዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ(1434-1468)ና ዐፄ ገላውዴዎስ(1540-1559) ወታደሮች የዘፈኗቸውና ‹የወታደሮች ዘፈኖች› የሚባሉትን ግጥሞች ስናይ አማርኛ በመካከለኛው ዘመን ይበልጥ እየዳበረ መምጣቱን ያሳያል፡፡ በዚህ ጊዜ በብዙ የቋንቋው ጥናት ሊቃውንት ግምት ውስጥ የማይገባውና ለአማርኛ ደቡባዊ ዕድገት የማይናቅ አስተዋጽዖ ያደረገው የሀገራዊ ትምህርቱ ማዕከል ወደ ደቡብ እየተቀየረ መምጣት ነው፡፡
 እስከ ቅድመ 12ኛው መክዘ ድረስ የሀገራዊ ትምህርት ማዕከላት የሆኑት ‹ሰሜን ሴማዊ› ቋንቋዎች የሚነገሩባቸው ትግራይና ኤርትራ ነበረ፡፡ አብዛኞቹ ገዳማትና አድባራት፣ ምሁራንና ሊቃውንት የነበሩት እዚያ ነው፡፡ መጻሕፍት ይጻፉና ይተረጎሙ የነበረውም እዚያው ነው፡፡
የአኩስም ዘመን በ8ኛው መክዘ አካባቢ ሲዳከም ከምእተ ዓመታት በኋላ አቡነ ኢየሱስ ሞአ አምሐራ እየተባለ ይጠራ በነበረው አካባቢ የሐይቅ እስጢፋኖስን ትምህርት ቤት በ1243 ዓም አካባቢ ሲጀምሩ የትምህርት ማዕከሉ ወደ ሀገረ አምሐራ መጣ፡፡ በዚህም የተነሣ ሐይቅን ተከትሎ ወለቃ ሌላው የትምህርት ማዕከል ሆነ፡፡ ወለቃ – ሐይቅም ደቡቡን ከሰሜን የሚገናኝ የትምህርትና የባሕል ድልድይ ሆነ፡፡ የ13፣ 14ና 15ኛው መክዘ ቅዱሳን ገድላትን ስንመለከት ይህን ይገልጡልናል፡፡ ይህ መሥመር ደግሞ አማርኛ የሚናገር ማኅበረሰብ የነበረበት በመሆኑ አማርኛ ቋንቋ ይበልጥ እንዲያድግ ረድቷል፡፡ ግእዝ ላዕላዩን ቦታ ቢይዝም ግእዝን በአማርኛ መማርም አንደኛው መንገድ ነበር፡፡  
በ13ና 14ኛው መክዘ በበጌምድር፣ በጎጃም፣ ሐረርጌና በደቡብ የተደረጉትን የክርስትና ማስፋፋቶችና የገዳማትና ትምህርት ቤቶች አተካከል ስንመለከት የአርጎባን፣ የጋፋትን፣ የዛይን፣ የሐረሪንና ሌሎች ሴማውያን ቋንቋዎችን ዱካ ተከትሎ እናገኘዋለን፡፡ የዚህ ዝምድና ጉዳይ ይበልጥ ሊጠና የሚገባ ይመስለኛል፡፡ በ14ኛውና በ15ኛው መክዘ ደብረ ሊባኖስና ከገዳሙ ጋር በተተያያዘ ታሪክ የተመሠረቱት የሸዋ፣ የጎጃም፣ የጎንደርና የወሎ አካባቢዎች የአማርኛ ቋንቋ ዋና መነገሪያዎች ሆነው እናገኛለን፡፡ የመጀመሪያዎቹን የአማርኛ ጽሑፎችንም የምናገኘው በዚህ አካባቢ ነው፡፡ በተለይ እነዚህ የትምህርትና የገዳማዊ ሕይወት ማዕከላት ከአርጎባ፣ ከዳሞትና ከጋፋት ሕዝቦች ጋር የነበራቸው ግንኙነት እንደገና ማጥናቱ የቋንቋው ዕድገት ከትምህርት ማዕከላትና ከሌሎች ሴማውያን ቋንቋዎች ጋር ያለውን ትግግዝ ያሳየናል፡፡ በዚህ ረገድ ታደሰ ታምራት በጋፋት ላይ የሠሩት ምሳሌ የሚሆን ነው (Taddesse Tamrat, 1988)፡፡
3.  ከ16ኛው መክዘ እስከ ዘመነ ቴዎድሮስ
በ16ኛው መክዘ አካባቢ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት የካቶሊክ ሚስዮናውያን ከኦርቶዶክስ ሊቃውንት ጋር የነበራቸው ክርክር አማርኛ ቋንቋን በሁለት መንገድ ጠቅሞታል፡፡ በአንድ በኩል ሚስዮናውያኑ ከነባሩ ግእዝ ይልቅ አማርኛ ቋንቋን ለሃይማኖት ትምህርት ማስተማሪያነት ተጠቀሙበት(አምሳሉ አክሊሉ፣ 1975)፡፡ በዚህም አማርኛ የማስተማሪያ ቋንቋ ሆነ፡፡ ይህንን ተከትሎም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትም በአማርኛ ማስተማር ጀመሩ፡፡ ይኼ ለሕዝቡ በአማርኛ ማስተማር አድጎና ዳብሮ በኋላ ላይ ወደ ትምህርት ማዕከላት በመግባት ጎንደር ላይ አንድምታ ትርጓሜው ንባቡ በግእዝ ትርጓሜው በአማርኛ እንዲሆን ያስቻለውም ይኼው ሂደት ነበር፡፡
 በሌላም በኩል ሚስዮናውያን መልእክቶቻቸውን በአማርኛ ቋንቋ እየጻፉ በማስተላለፋቸው ነባር ሊቃውንትም በአማርኛ ቋንቋ መልስ መስጠት ጀመሩ፡፡ ይኼ ሂደትም አማርኛን የሃይማኖት ትምህርት መጻፊያ ቋንቋ እንዲሆን አስቻለው፡፡ በተለይም ፓኤዝ ብዙ የካቶሊክን እምነት የሚገልጡ መጻሕፍት ወደ አማርኛ እንዲተረጎሙ አደረገ (The missionary Factor, Merid Wolde Aregay, 47, 1996)፡፡ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትም ለዚህ አዲስ እንቅስቃሴ መጻሕፍትን ከግእዝ በመተርጎምና በአማርኛ አዳዲስ መጻሕፍትን በመጻፍ መልስ ሰጡ፡፡ እነ አንቀጸ አሚን፣ ጠቢበ ጠቢባን፣ ሥነ ፍጥረት፣ ምሥጢረ ጽጌያት ከግእዝ ወደ አማርኛ የተተረጎሙት በዚህ ዘመን ነበር ((Nostnitisn, 2003, 238)::  እነ ‹ነገረ ሃይማኖት›ና ‹ትምህርተ ሃይማኖት›ም ተዘጋጁ(Getachew Haile, 1980)፡፡ በጀርመን ሚሲዮናውያን አማካኝነት የዮሐንስ ወንጌል ወደ አማርኛ ተተርጉሞ በ1647 ታተመ (አምሳሉ አክሊሉ፣ 1976)፡፡ ሉዶልፍም የአማርኛ ሰዋስውን በ1698 አሳተመ፡፡ ከ16ኛው መክዘ ወዲህም በኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ዘንድ የአማርኛ ሰዋስውን መጻፍ ተጀመረ(Getachew Haile, 1970)::
ምንም እንኳን የቃል መረጃዎችና አንዳንድ መዛግብት (EMML 2117) የአማርኛ የአንድምታ ትርጓሜ ቀደም ያለ ታሪክ እንዳለው ቢገልጡም ንባብ በግእዝ፣ ትርጓሜ በአማርኛ ሆኖ ይበልጥ መሰጠት የጀመረው ግን በ17ኛው መክዘ እና በ18ኛው መክዘ በጎንደር ነው፡፡   
ከዚህም በተጨማሪ ምንም እንኳን ግእዝ የትምህርትና የሥነ ጽሑፍ ቋንቋነቱን እንደጠበቀ ቢሆን፣ በብራና መጻሕፍት ላይ አማርኛና ግእዝ ጎን ለጎን መታየት የጀመሩት ከ17ኛው መክዘ በኋላ ነው፡፡ ግእዝ ዋናውን የጽሑፍ ቦታ (ገድሉና፣ ዜና መዋዕሉን፣ ጸሎቱን፣ ወዘተ) ሲይዝ አማርኛ ደግሞ የዕለት ተዕለት ማኅበራዊ ኑሮውን ቦታ ያዘ፡፡ በጎንደር ዙሪያ አድባራት የምናገኛቸው የ17ኛው፣ 18ኛውና ከዚያ በኋላ ያሉት መጻሕፍት በኅዳጋቸው የሚጽፉት የውርስ፣ የርስት፣ የሽያጭና ግዥ፣የውልደት፣ መዛግብት በአማርኛ ቋንቋ የሚጻፉ ናቸው፡፡ ይህም አማርኛ ከግእዝ ቀጥሎ የጽሑፍ ቋንቋነቱ እያደገና በቤተ ክህነቱና በቤተ መንግሥቱ ጸሐፍትም ዘንድ ተቀባይነት እያገኘ መምጣቱን ያሳየናል፡፡ በዘመነ መሳፍንት የነበሩት እነ ራስ ዓሊ፣ ደጃች ውቤ፣ ደጃች ጎሹ፣ ይጻጻፉ የነበረው በአማርኛ እንደነበረ ዛሬ ለዘር ተርፈው ያገኘናቸው ደብደቤዎቻቸው ያሳዩናል(Rubenson, 1987)
የዐፄ ቴዎድሮስ ወደ ሥልጣን መምጣት ለአማርኛ ቋንቋ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል፡፡ በአንድ በኩል ዜና መዋዕላቸው በአማርኛ እንዲጻፍ ማድረጋቸው ግእዝ ይዞት የነበረውን አንድ የሥነ ጽሑፍ መንገድ አማርኛ እንዲረከበው አደረጉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የቤተ መንግሥቱን የሥራ ግንኙነት በንጉሥ ደረጃ በአማርኛ መጻፍ መጀመራቸው ግእዝ የፕሮቶኮል ቋንቋነቱን ለአማርኛ እንዲያስረክብ አደረገው፡፡ (የዐፄ ቴዎድሮስ ደብዳቤዎች Sven Rubenson, Acta Aethiopica, vol. II)በርግጥ በዚህ ጉዳይ ላይ የሸዋው ንጉሥ ሣሕለ ሥላሴም በአማርኛ የመንግሥቱን የመጻጻፍ ሥራ በመሥራት ታሪኩን ይጋራሉ፡፡ የደብተራ ዘነብ መጽሐፈ ጨዋታ ሥጋዊ ወመንፈሳዊም የዚህ ዘመን ፍሬ ነው፡፡ ደብተራ ዘነብ የጻፉት የቴዎድሮስ ታሪክ፣ የኢዘንበርግ የዓለም ታሪክ(1842) እና የአማርኛ የጂኦግራፊ መጽሐፍ (1842) የዚህ ዘመን ማስታወሻዎች ናቸው፡፡ የእንግሊዝ የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበርም በ1842 የአርባዕቱን ወንጌል የግእዝና አማርኛ እትም አሳተመ (Pankhurst, 1976,3110)::
4. ከዘመነ ቴዎድሮስ እስከ ዘመነ ምኒሊክ
ዐፄ ዮሐንስ ዐፄ ቴዎድሮስ የጀመሩትን፣ ንጉሥ ሣሕለ ሥላሴ ቀደም የበረቱበትን፣ የቤተ መንግሥቱን ሥራ በአማርኛ ቋንቋ ማከናወንን አጠንክረው ቀጠሉበት፡፡ የዐፄ ዮሐንስ ደብዳቤዎቻቸው በአማርኛ ይጻፉ ነበር፡፡ (Rubenson, 2000)
አማርኛ ይበልጥ የመስፋፋትና የማደግ ዕድሉን ያገኘው በዐፄ ምኒሊክ ዘመን ነው፡፡ ዐፄ ምኒሊክ እንደ ቴዎድሮስና ዮሐንስ ሁሉ አማርኛን የቤተ መንግሥቱ የሥራ ቋንቋ አድርገውታል፡፡ ይህንንም የዐፄ ምኒሊክን ዐዋጆች (ጳውሎስ ኞኞ፣ ዳግማዊ ዐጤ ምኒሊክ፣1984) ደብዳቤዎቻቸውንም (ጳውሎስ ኞኞ፣ የምኒሊክ ደብዳቤዎች፣2003) መመልከቱ ጠቃሚ ነው፡፡ ይህ ዘመን ለአማርኛ ሦስት ዕድሎችን አምጥቷል፡፡ 
የመጀመሪያውየዐፄ ምኒሊክ የመንግሥት ሥልጣን ወደ ደቡብ፣ ምዕራብና ምሥራቅ መስፋፋቱ አማርኛ በእነዚህ አካባቢዎች ይበልጥ እንዲስፋፋ ረድቶታል፡፡ አማርኛ በእነዚህ አካባቢዎች ቀድሞ ከነበረበት ቦታ ላቅ ባለ ሁኔታ መስፋፋት ብቻ ሳይሆን ከእነዚህ አካባቢዎችም ብዙ ጠባዮችን እንዲወስድ ሆኗል፡፡ ሁለተኛው ዕድል አማርኛ የጋዜጣ፣ የሥነ ጽሑፍና የፍርድ ቋንቋ መሆኑ ነው፡፡ አእምሮ ጋዜጣ የታተመው በአማርኛ ነው፡፡ ጦቢያ ልቦለድ የተጻፈው በአማርኛ ነው(1908)፤ የምኒሊክ ዐዋጆችና የዘመኑ ፍርዶች የሚሰጡትና የሚጻፉት በአማርኛ ነው፡፡ ሦስተኛውዕድል ደግሞ አማርኛ በትምህርት ደረጃ መሰጠት መጀመሩ ነው፡፡ በዐፄ ምኒሊክ ዘመን በተከፈተው የዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት አማርኛ በትምህርትነት መሰጠት ጀመረ፡፡ ይኼም ለአማርኛ ሰዋስውና ሥርዓተ ጽሕፈት ማደግ አስተዋጽዖ አድርጓል፡፡ በርግጥ በዚህ ረገድ ሚሲዮናውያን ከምኒሊክ ዘመን ቀደም ብለው የመሠረቱን ድንጋይ ጥለዋል፡፡ ትምህርት ቤት በከፈቱባቸው ቦታዎች ሁሉ የአማርኛ ቋንቋን ያስተምሩ ነበር፡፡ ለምሳሌ ላዛሪስቶች በ1870ና 80ዎቹ በከረንና አካባቢው በከፈቷቸው ትምህርት ቤቶች አማርኛ ማንበብና መጻፍ ያስተምሩ ነበር (Pankhurst, 1976,314)::
5. ከዘመነ ምኒሊክ እስከ አሁን
አማርኛ ከዐፄ ምኒሊክ ዘመን በኋላ የመንግሥት የሥራ ቋንቋ፣ ብሔራዊ ቋንቋ፣ የሚዲያና የኅትመት ቋንቋ፣ የሥነ ጽሑፍና የማስተማሪያ ቋንቋ ሆኗል፡፡ ከዐረብኛ ቀጥሎ በስፋት የሚነገር ሴማዊ ቋንቋ የሆነው አማርኛ (Girma, 2009, 2) በአሁኑ ዘመን ከ80 በመቶ በላይ በሚሆነው ኢትዮጵያዊ ዘንድ የመጀመሪያ ወይም ሁለተኛ ቋንቋ ሆኖ ይነገራል (Ibid; Meyer and Richter, 40):: የአማራ፣ የደቡብ፣ የጋምቤላና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች፣ የአዲስ አበባና የድሬዳዋ መስተዳድሮች የሥራ ቋንቋ ነው፡፡ በእሥራኤል ከ80 ሺ በላይ ተናጋሪዎች አሉት፡፡ በአሜሪካ፣ በአውሮፓ፣ በእስያና በአፍሪካ የሚገኙ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን ይናገሩታል፡፡ በዋሽንግተን ዲሲ ከተናጋሪው መብዛት የተነሣ የከተማው መንግሥት እንደ አንድ የመሥሪያ ቋንቋ ተቀብሎታል፡
ተግዳሮቶቹና የመፍትሔ ሐሳቦች
1.     ተቋማዊ ባለቤት የሌለው መሆኑ
የአማርኛ ቋንቋን የሚያጠና፣ ደረጃዎችን የሚያወጣ፣ አዳዲስ ቃላትን የሚመዘግብ፣ ስያሜ ቃላትን የሚያዘጋጅ እኔ ባይ ተቋም የለውም፡፡ ግእዝን በዚህ ረገድ የጠቀመው ሁለት ነገር ነው፡፡ በአንድ በኩል እኔ ባይ ተቋም ቤተ ክህነት አለቺው፡፡ በሌላም በኩል ደግሞ በትምህርትነት ከጥንት ጀምሮ ይሰጣል፡፡ እኔ ባይ ተቋም መኖሩ ዕውቀቱ እንዲከማች፣ እንዲጠበቅና እንዲዳብር አድርጎታል፡፡ በትምህርትነት መሰጠቱ ደግሞ ሕግና ሥርዓቱ የታወቀና የተረዳ እንዲሆን፣ ደረጃውና መልኩ በተግባቦት ደረጃ እንዲታወቅ ረድቶታል፡፡
ለእንግሊዝኛ ኦክስፎርድና ካምብሪጅ በእንግሊዝ፣ ሐርቫርድ በአሜሪካ የዋሉለትን ውለታ ለአማርኛ በኢትዮጵያ ውስጥ  የሚውልለት ተቋም የለውም፡፡ ሲቋቋም ከሌሎች ጋር ተደርቦ ወይም ‹የኢትዮጵያ ቋንቋዎች› በሚል ተከብቦ ነው፡፡ የመዝገበ ቃላት ዝግጅቱን እንኳን ስናየው በየጊዜው የሚጨምር፣ የሚሻሻልና ቅደም ተከተል (Series) ያለው አይደለም፡፡ የቋንቋ አካዳሚዎችም አንዴ አንድ ሥራ ይሠራሉ ከዚያ ያቆማሉ፡፡ በየጊዜው የሚፈጠሩትን ቃላት መዝግቦ ለመዝገበ ቃላት የሚያበቃ እንደ ማርያም ዌብስተር ያለ አላገኘም፡፡ ስያሜ ቃላት ሲያስፈልጉ የሚጠየቅ፣ በቋንቋው ላይ የሚደረጉ ጥናቶችን የሚያከማች፣ እኔ ባይ ተቋም አላገኘም፡፡
በመሆኑም ልክ እንደዚህ አሁን እንደተሰበሰብንበት ያለ ቋንቋውን ማጥናትና ማበልጸግ ዋና ዓላማው የሆነ ምሁራዊና ሳይንሳዊ ተቋም ያስፈልጋል፡፡ ተቋሙም እንዲሁ ዐጽመ ስም ያለው ብቻ ሳይሆን በአካዳሚያዊ ነጻነት የሚሠራ፣ ለውጥ ለማምጣት የሚተጋ የዕውቀት ቦታ መሆን ይገባዋል፡፡ ሌሎች የግልና የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎችና ተቋማትም ይህንን መሰል አካላትን እየፈጠሩ በተለይም በሴማዊ ቋንቋዎች(አንዳንዶቹ እየጠፉ በመሆኑ) ላይ ጥናት ማድረግና በአብዛኛው ከሀገሪቱ ውጭ የሚደረገውን የሴማዊና ኦርየንታል ጥናትን ወደ ሀገሪቱ ማምጣት አለባቸው፡፡  
2.  ቅቡልነት ያለው መለኪያ አለመኖር
አማርኛን በመጻፍና በመናገር ረገድ ሀገራዊ ቅቡልነት ያለው የአሠራር ደረጃ አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ አንድን ሥነ ጽሑፍ በእንግሊዝኛ ስንጽፍ ሥርዓቱን በተመለከተ የሚመሩን የታወቁ ደረጃዎችና ደረጃ አውጭዎችም አሉ፡፡ በዚህ ረገድ የቺካጎ ማኑዋል ተጠቃሽ ነው፡፡ ድርጅቶች፣ የትምህርት ተቋማትና የኅትመት ተቋማት ሥራችሁን በዚህ ደረጃ መሠረት አቅርቡ ይላሉ፡፡ አማርኛ ግን ሀገራዊ ቅቡልነትን ያተረፈ ደረጃ አውጭም ሆነ ደረጃ አለው ለማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ ይህ መሆኑ ደግሞ አጠቃቀማችን አንድ ወጥ እንዳይሆን፣ በተለይም በትምህርት ተቋማት የሚሰጠው የቋንቋ ትምህርት እንደየመምህሩ እንዲለያይ አድርጎታል፡፡ ሚዲያዎቹም አንድ ወጥ የሆነ አጠቃቀም እንዳይከተሉ መረን ለቋቸዋል፡፡ በተለይ በሁለተኛ ቋንቋነት ለሚማረው ሰው ደግሞ እጅግ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ በርእስ፣ በዐንቀጽ፣ በመረጃ አሰጣጥ፣ በዋቤ አመዘጋገብ፣ በግርጌ ማስታወሻ አሰጣጥ፣ በፊደል መጠን፣ ወዘተ አንድ የሚያግባባ ደረጃ ያስፈልገን ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ የአጻጻፍ ሥርዓቱ ወጥ እንዲሆን ባለመሠራቱ ‹ጠዋት፣ ጥዋትና ጡሃት›፣ ‹መስተዋትና መስታውት›፣ የመሳሰሉትን ለመተራረም እንኳን አቅቶናል፡፡
ምሁራን፣ ተቋማት፣ መንግሥታዊ አካላትና ሌሎች ከተግባቦት ላይ የሚደርሱበት፣ በዕውቀታዊና ምሁራዊ ደረጃው፣ በባሕላዊና ማኅበራዊ ዐቅሙ ከፍ ያለ የአማርኛ ቋንቋ ሥርዓተ ጽሕፈት፣ መልክዐ ፊደል፣ ሰዋስው፣ ስያሜ ቃላት፣ የመጻሕፍት፣ የጥናታዊ ወረቀቶች፣ የማስታወቂያዎች፣ የዜናዎች፣ ወዘተ አጻጻፍ ደንብ ሊኖረን ይገባል፡፡ ይህንን የሚጠኑ፣ የሚተገብሩና የሚከታተሉ ተቋማትም ያስፈልጋሉ፡፡ በየጊዜውም ማንዋሎችን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ 
3.  ቋንቋውን ሰው ወይም ሥርዓት ማድረግ
በተለይ ከቅርብ ዘመናት ወዲህ አማርኛን ይናገሩ የነበሩ ሥርዓቶችና የሥርዓት መሪዎች ለሚፈጥሩትና ለፈጠሩት ችግር አማርኛ ቋንቋም አብሮ ተጠያቂ እየሆነ ነው፡፡ የሥርዓት መስፋፋት ለቋንቋ መስፋፋት ፣ የቋንቋ መስፋፋትም ለሥርዓት መስፋፋት መጥቀማቸው የየትም ሀገር ነባራዊ ሁኔታ ነው፡፡ በእንግሊዝ ግዛት ፀሐይ አትጠልቅም ባይባል ኖሮ እንግሊዝኛ በተአምር የዓለም መነጋገሪያ ባልሆነ ነበር፡፡ እንጂማ የቻይና ቋንቋ በተናጋሪዎች ብዛት እንግሊዝኛን ይበልጠው ነበር፡፡ የእስልምናና የዓረብ ግዛት መስፋፋት ለዐረብኛ ቋንቋ መስፋፋትና ማደግ ያበረከቱትን አስተዋጽዖ ማንም አይክደውም፡፡ እነ ፈረንሳይኛና ስፓኒሽ ያለ ግዛት መስፋፋት አልተስፋፉም፡፡ አማርኛም እንዲሁ ነው፡፡
ዛሬ እንግሊዝኛ

የምታስፎክር ሰንጋ ገለሌ
በጦር መካከል ሳይሆኑ አያሌ
በጥይት ገዳይ ነጭ ብርገድሌ
የሴት ወንድ ናት ሸዋረገድ ገድሌ
ተብሎ የተገጠመላቸውን፣ በአምስት ዓመቱ የጠላት ወረራ ጊዜም አኩሪ ጀብዱ የፈጸሙትን የአርበኛዋን የሸዋረገድ ገድሌን ታሪክ የሚተርክ መጽሐፍ ሰሞኑን ቀርቧል፡፡ ‹ሸዋ ረገድ ገድሌ፣ የአኩሪ ገድላት ባለቤት ይሰኛል፡፡ ሺበሺ ለማ ጽፎት ዶክተር ክፍሌ ማርቆስ ገድሌ አሳትመውታል፡፡
በአምስት ዓመቱ የፋሽስት ወረራ ጊዜ ለሀገራቸው አኩሪ ገድል በመፈጸምና ለነጻነታችን ዋጋ በመክፈል ስማቸው ከሚነሡ ሴቶች ሸዋረገድ ገድሌ ግንባር ቀደም ናቸው፡፡ በ1878 ዓም የተወለዱት ወ/ሮ ሸዋ ረገድ ገድሌ ሁለገብ እንደነበሩ ታሪካቸው ያሳያል፡፡ የቤተ ክህነቱን ትምህርት ተምረዋል፡፡ ትዳርን አልፈልግም ብለው ምናኔን መርጠው ኢየሩሳሌም ድረስ ተጉዘዋል፡፡ ከመጀመሪያዎቹ የባንክ ተጠቃሚዎች፣ የአክሲዮን ገዥዎች፣ የፋብሪካ ተካዮች መካከል አንዷ ነበሩ፡፡ የጉለሌ ቅዱስ ገብርኤልንም ያስተከሉት እርሳቸው ነበሩ፡፡ 

የሸዋረገድን ስም ይበልጥ ከፍ አድርጎ ያስጠራው አርበኛነታቸው ነው፡፡ የኢጣልያ ጦር ሊጎርሰን ማሰፍሰፉ ሲሰማ በአዲስ አበባ ከተማ በሀገር ተቆርቋሪ ዜጎች በተቋቋመው የሀገር ፍቅር ማኅበር አባልነት መጀመሪያ ከተመዘገቡት ጥቂት ሴቶች መካከል አንዷ እርሳቸው ነበሩ፡፡ ወራሪው ፋሽስት አዲስ አበባ ሲገባና የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ወርዶ የኢጣልያ ባንዴራ ሲተካ ወ/ሮ ሸዋረገድ ገድሌ ስቅስቅ ብለው አለቀሱ፡፡ በዚህ ምክያትም በኋላ  ‹የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ወርዶ የገናናው የኢጣልያ ሰንደቅ ዓላማ ሲውለበለብ በማየትሽ አልቅሰሻል›› በሚል ተከሰው ነበር፡፡ ሸዋረገድም ያለምንም ፍርሃት ‹አዎ አልቅሻለሁ፤ ያገሬን መወረርና መዋረድ ያወቅሁት የኛ ሰንደቅ ዓላማ ወርዶ የናንተ ሲውለበለብ በመታየቱ ነው፡፡ ሰው ለእናት ሀገሩ ቢያለቅስ ነውሩ የት ላይ ነው?›› ብለው ነበር የመለሱት፡፡ 
 
ወ/ሮ ሸዋረገድ ለአርበኞች ስንቅ በማቀበል፣ መሣሪያ በመግዛት፣ መረጃ በማሰባሰብ፣ መድኃኒት በመላክና ሞራል በመስጠት አምስቱን ዓመት በተጋድሎ ነው ያሳለፉት፡፡ በዚህ ምክንያት በተከሰሱ ጊዜም ‹‹ለአርበኞች ስንቅ ማቀበሌ እውነት ነው፤ይህንንም ያደረግኩት ለሀገሬ ክብር ብዬ ነው፡፡ ሰው እንኳን ለሀገሩ የእናንተ ወይዛዝርት ሀገራቸው ያልሆነቺው ኢትዮጵያን ለመውረር የጣታቸውን ቀለበት ሳይቀር መስጠታቸውን ትናገራላችሁ፡፡ እኔም ለሀገሬ የሠራሁት ሲያንሰኝ እንጂ አይበዛብኝም›› ነበር ያሉት፡፡
ወ/ሮ ሸዋረገድ ከሚጠቀሱላቸው ሥራዎቻቸው አንዱ ለቀይ መስቀል ማኅበር የነበራቸው ድጋፍ ነው፡፡ በጦርነቱ ዋዜማ ሐምሌ 1 ቀን 1927 ዓም ለተቋቋመው የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ንብረታቸውን ሸጠው አስረክበዋል፡፡ እሥር ቤት በገቡ ጊዜ ከተከሰሱበት ወንጀል አንዱም ‹ቀይ መስቀልን ትረጃለሺ› የሚል ነበር፡፡ ሸዋረገድ ቀይ መስቀልን ከመርዳትም ባሻገር ኢትዮጵያውያን ወይዛዝርት እራፊ ጨርቅ እንዲያሰባስቡ በማድረግ ለአርበኞች ቁስል ማሸጊያ ይልኩላቸው ነበር፡፡ 
 
ሸዋረገድ ከርዳታው ጎን ለጎን ለአርበኞቹ የመረጃ ምንጭም ነበሩ፡፡ በከተማው የሚገኙ የጠላት መረጃዎችን በማሰባሰብና ወደ አርበኞች በምሥጢር በመላክ አርበኞች እንዲጠቀሙባቸው አድርገዋል፡፡ በዚህና በሌሎች ገድሎቻቸው ምክንያትም የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው ነበር፡፡ በፈጣሪ ቸርነት ግን ሳይፈጸምባቸው ቀርቷል፡፡ የሞት ፍርዱ ባይፈጸምባቸውም የኢጣልያን እሥር ቤት ከሚያዘወትሩት አንዱ ሸዋረገድ ሆነዋል፡፡ በየጊዜው ይታሠራሉ፤ ይፈታሉ፡፡ በመጨረሻ ግን አዚናራ ወደምትባል ከሰርዲኒያ ሰሜናዊ ምዕራብ ወደምትገኝ ደሴት ታሥረው ተልከዋል፡፡ 
 
እዚያም ቢሆን ጽናታቸው አልተሰበረም፤ ወኔያቸውም አልተሰለበም፡፡ የሚያደርጉት ቢያጡ በእሥር ቤት የሚቀርብላቸውን የተበላሸ ምግብ በአሣሪዎቻቸው ፊት በመድፋትና ጦማቸውን በመዋል ፋሽስትን ይቃወሙ ነበር፡፡ በዚህ ሁኔታም ለአንድ ዓመት ከመንፈቅ ታሥረው ተፈቱ፡፡ አዲስ አበባ ሲገቡ ግን ትግላቸውን ቀጠሉ እንጂ አላቆሙም፡፡ ሕዝቡም
 
የዘበኛ ሱሪ ካኪና ገምባሌ
እንኳን ደኅና መጣሺ ሸዋረገድ ገድሌ
 ብሎ ተቀበላቸው፡፡ 
 
በተለይም በጅቡቲ የነበረ አንድ ኢትዮጵያዊ የሰጣቸውን ‹የይሁዳ አንበሳ› የሚል ጽሑፍና ዓርማ ያለበትን ወረቀት ከንጉሡ የተላከ የሚመስል መልእክት እየጻፉ ወደ በረሐ በመላክ አርበኞችን አበረታተውበታል፡፡ የአዲስ ዓለም የጣልያን ምሽግ ኅዳር 5 ቀን 1933 ዓም በአርበኞች ሲሰበር ዋናውን መረጃ የሰበሰቡትና ዐቅድ የነደፉት ሸዋረገድ ነበሩ፡፡ ከምሽጉ ሰበራ በኋላም ደጀን መሆኑን ትተው ራሳቸው ወደ ውጊያ ዐውድማ ገቡ፡፡ በተለይም መቂ አካባቢ ከሻለቃ በቀለ ወያ ጦር መካከል ተሰልፈው ተዋግተዋል፡፡ በኋላም ጅማ አካባቢ ከነበረው ከገረሱ ዱኪ ጦር ጋር ለመገናኘት ተጓዙ፡፡ በዚያ እያሉም ጠላት ድንገተኛ አደጋ ጥሎ ገጠማቸው፡፡ ለአራት ሰዓት ያህልም ተዋግተው ተማረኩ፡፡ ወደ እሥር ቤት ተወስደውም የፊጥኝ ታሠሩ፡፡ 
 
በ1933 ዓም ሀገሪቱ ከፋሽስት ኢጣልያ ወረራ ነጻ ስትወጣ ሸዋረገድ ገድሌ አርበኞችን ወደመርዳትና የበጎ አድራጎት ሥራን ወደ መሥራት ገቡ፡፡ በንግዱም መስክ ተራመዱ፡፡ ሀገራቸውን እስኪበቃቸው አገልግለው፤ ግሼን ማርያም ሄደው ሥጋወደሙን ተቀብለው፤ ከዚያም ወደ ላሊበላ ተጉዘውና ተሳልመው፤ የመጨረሻቸው መሆኑን እየተናገሩ ጥቅምት 22 ቀን 1942 ዓም ዐረፉ፡፡ ሕዝቡም 
 
እናንት ወጥ ቤቶች በርበሬ ቀንጥሱ
እናንት ሥጋ ቤቶች ሰንጋውን ምረጡ
ሸዋረገድ ገድሌ ለገና ሲመጡ፡፡
ቤተሰቧ ሰፊ ገናና ጥምቀት
ሸዋረገድ ገድሌ እንደምን ትሙት፡፡ ብሎ ገጠመላቸው፡፡ 
 
ሰፊ ነው ታሪካቸው፡፡ ልብ የሚያሞቅ፤ ወኔ ቀስቃሽ፤ አስደማሚ፤ ከዐለት የበረታ ጽናት፤ ከእቶን የጋለ አርበኝነት፤ ከትንታግ የተንቀለቀለ የሀገር ፍቅር ታገኙበታላችሁ፡፡ ምናለ አደባባዮቻችን በንግድ ኩባንያዎች ስም ከሚጠሩ በነ ሸዋረገድ ገድሌ ስም ቢሰየሙ ብላችሁም ትቆጫላችሁ፡፡

 

ኢያን ካምፕቤል ፋሽስት ኢጣልያ ኢትዮጵያን በወረረች ጊዜ በደብረ ሊባኖስ ገዳም ላይ ስለ ፈጸመቺው አሰቃቂ እልቂት የሚተርክ The Massacre of Debre Libanos, Ethiopia 1937› የተሰኘ መጽሐፍ አሳትመዋል፡፡ ይኼ ብዙ ጊዜ የማይነገርለት ነገር ግን እርሳቸው ‹ፋሽዝም ከፈጸማቸው ጆሮ ጭው የሚያደርጉ የጭካኔ ሥራዎች አንዱ ነው› ብለው የገለጡት ዘግናኝ የሃያኛው ክፍለ ዘመን ሰብአዊ አረመኔነት በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በጥናት ተመሥርቶ በዝርዝር ቀርቧል፡፡ 

ጣልያኖች የኢትዮጵያውያንን የጀግንነት መንፈስ ለመስበር ከመጀመሪያው ተዘጋጅተው ነበር የመጡት፡፡ ለዚህ ደግሞ እንደ አንድ ርምጃ የወሰዱት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ማንበርከክ ነው፡፡ ምንም እንኳን የተወሰኑ ጳጳሳት ከእነርሱ ጋር ለመሥራት ባያንገራግሩም እንደ አቡነ ጴጥሮስ ያለ ቆራጥ አባት መፈጠሩ፤ ብዙዎች ገዳማትና አድባራት አርበኞችን መርዳታቸው፤ ካህናቱም
ወግጅልኝ ድጓ ወግጅልኝ ቅኔ
ወንዶች ከዋሉበት እውላለሁ እኔ
እያሉ ሀገራቸውን ለመከላከል በረሐ መውረዳቸው ጣልያኖችን ዕረፍት ነሥቷቸው ነበር፡፡ በተለይም ደግሞ የካቲት 12 ቀን 1929 ዓም በግራዝያኒ ላይ በተቃጣው የመግደል ሙከራ ዋነኞቹ ተሳታፊዎች አብርሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ጋር ግንኙነት አላቸው መባሉ፡፡ አርበኛው ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ የፍቼ ተወላጅ በመሆናቸው ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ጋር ግንኙነት አላቸው ተብሎ በመታሰቡ፡፡ ታዋቂው አርበኛ  ኃይለ ማርያም ማሞ  ከገዳሙ መነኮሳት ጋር ይገናኛል መባሉ ጣልያኖች በደብረ ሊባኖስ ላይ የዘንዶ ዓይናቸውን እንዲጥሉ አደረጋቸው፡፡ 
ይበልጥም ደብረ ሊባኖስ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለው ቦታ የጣልያኖችን የጥፋት ትኩረት ስቦታል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱን፣ በእርሷም በኩል የጀግንነቱን መንፈስ አከርካሪውን ለመስበር ያሰቡት ፋሽስቶች የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ምዕራፍ፣ የእጨጌው መቀመጫና ለአያሌ ገዳማት መመሥረት ምክንያት የሆነውን ገዳም ለማጥፋት፣ ሲያጠፉትም ሌላውን ሊያስደነግጥ በሚችል መልኩ በአሰቃቂ ሁኔታ እንዲሆን ወሰኑ፡፡
በዚህም መሠረት ግራዝያኒ ያቀናበረውና ጄኔራል ማለቲ የመራው ጦር ግንቦት 10 ቀን 1929 ዓም ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ወረደ፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐጽም የተከናወነበትን በዓል ለማክበር የተሰበሰቡትን ምእመናንንና መነኮሳትን መጨፍጨፍም ጀመረ፡፡ በጫጋል፣ በውሻ ገደል፣ በሥጋ ወደሙ ሸለቆና በደብረ ብርሃን አጠገብ በእንግጫ በተከናወነው ጭፍጨፋ ገና ነፍስ ያላወቁ ሕጻናት የቆሎ ተማሪዎችን ጨምሮ ከ1801 እስከ 2201 የሚደርሱ ምእመናንና መነኮሳት በግፍ ተረሸኑ፡፡ አውሬ እንዲበላቸውም የትም ተወረወሩ፡፡
በዚህም አላበቃም፡፡ በገዳሙ የነበሩ መጻሕፍት፣ የከበሩ ዕቃዎች፣ ንዋያተ ቅድሳት፣ ገንዘብና ሌሎች ንረቶች ተዘረፉ፡፡ ገዳሙም ነጻነት እስኪመለስ ድረስ በመከራ ውስጥ ኖረ፡፡
አስገራሚው ነገር ከ500 ዓመታት በፊት ግራኝ አሕመድ ገዳሙን ሲያቃጥል የሞቱት መነኮሳት ቁጥር 450 ነበር፡፡ ፋሽስት ኢጣልያ የጨፈጨፈቺው ከእርሱ አምስት ጊዜ እጥፍ የሚበልጥ መሆኑን ስናስበው የጭካኔውን መጠን ያመለክተናል፡፡
መጽሐፉን ስታነቡት ኀዘን፣ ቁጭትና ግርምት ይፈራረቁባችኋል፡፡ ሕጻናት፣ ወጣቶች፣ ጎልማሶችና አረጋውያን በሃይማኖታቸውና በኢትዮጵያዊነታቸው ምክንያት ብቻ የደረሰባቸውን ግፍ ስናስበው ልባችን በኀዘን ፍላጻ ይወጋል፡፡ ማንበብ እስኪያቅተን ድረስ በሰቆቃወ ደብረ ሊባኖስ እንዋጣለን፡፡ ለደረሰባቸው ግፍ ተመጣጣኝ ካሣ አለማግኘታቸውን፣ ኢጣልያ የፈረመቺውን ውል እንኳን ሳታከብረው 74 ዓመታት ማለፋቸው ስትመለከቱ፡፡ ግራዝያኒ ወስዷቸው ዛሬ እንደ አቤል ደም እየተካሰሱ በሮም የሚገኙትን የገዳሙን ንብረቶች ስታስታውሱ አባቶቻችን ልጅ አለመውለዳውን ዐውቃችሁ ይቆጫችኋል፡፡
ልጅ የለንም እንጂ ልጅማ ቢኖር
ተሟግቶም ተዋግቶም ያስመልስ ነበር፤
ብለው ያንጎራጎሩ ሲመስላችሁ ትቆጫላችሁ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ይኼ እኛ ዛሬ የምንቀልድበት ነጻነት ምን ያህል ዋጋ እንደተከፈለበት ስታስቡ፣ ዋጋ ከፋዮቹንም በዓይነ ኅናችሁ ስትቃኙ ትገረማላችሁ፡፡ ግርምታችሁ በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ በዚያ የመከራ ዘመን የሰማዕታቱን ዐጽም ለመሰብሰብ፣ ቦታቸውም ለማወቅ በመንፈሳዊና ሀገራዊ ወኔ ታጥቀው የከወኑትም፤ ለታሪክም አስረጅ ሆነው የቆሙትን የክፉ ቀን ጀግኖች ስታስቡም ትደነቃላችሁ፡፡ እግረ መንገዳችሁን እንዲህ ያሉት የዓይን ምስክር ጀግኖች በዐረፍተ ሞት ከመገታታቸው በፊት ሌላውም ታሪካችን እንዲጻፍ ትማጸናላችሁ፡፡ አብዛኛው ሕዝብ አንብቦ እንዲጠቀምበትም በአማርኛ ታሪኩ ቢቀርብ መልካም መሆኑንም ሐሳብ ትሠነዝራላችሁ፡፡
ከዚህም በላይ ደግሞ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ሁለት ሥራዎች እንደቀሩትም ትገነዘባላችሁ፡፡ ለእነዚህ ለእምነታቸውና ለሀገራቸው ሲሉ ለተሠዉ ሰማዕታት ተገቢውን ቦታ መስጠት፣ ታሪካቸውንም በስንክሳር ውስጥ በተገቢው ሁኔታ እንዲሠፍር ማድረግ፤ አያይዞም ደግሞ በዓላቸው በኦርቶዶክሳዊ ሥነ ሥርዓት እንዲከበርና ትውልድ ሀገራዊም መንፈሳዊም በረከት እንዲያገኝባቸው ማድረግ ይገባዋል፡፡ ለዚህም ደራሲው ኢያን ካምፕቤል አጥልቀው አጥንተው፣ ተንትነው ጽፈውታልና ምስጋና እየቸርን መጽሐፉን እናንብበው፡፡
መልካም ንባብ፡፡

በምሥራቅ ጎጃም ገበሬዎች ባሕል የኑግ ክምር አዳቦል ይባላል፡፡ የኑግ ክምር ቀላል በመሆኑ ነገረ ቀላል የሆነውን ሰው አዳቦል ይሉታል፡፡ እነርሱ አዳቦል የሚሉት ነገረ ቀላል ሰው ሦስት ነገሮች የሌሉትን ነው፡፡ ወይ ሲናገር አዲስ መረጃ የማይሰጠውን፣ ወይም ዕውቀት የማያዳብረውን ወይም ደግሞ ለሁኔታው የማይመጥን ነገር የሚናገርውን፡፡ 
በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ሐዲስ ዓለማየሁ የባሕል ማዕከል ዓመታዊ በዓል ምሽት ላይ በኛ ጠረጲዛ ዙሪያ የነበሩ ምሁራን ይህንን የገበሬውን ነገር ሲሰሙ አዳቦልነት በሦስት ነገሮች የተነሣ ሊመጣ ይችላል ሲሉ ሐሳብ ሠነዘሩ፡፡ የመጀመሪያው ለንግግርና ለጽሑፍ ካለመጠንቀቅ ነው፡፡ ለማን፣ ምን፣ እንዴት ልናገር ብሎ የማያስብና እንዳመጣለት ብቻ የሚናገር ወይም የሚጽፍ ሰው ንግግሩ ወይም ጽሑፉ አዳቦል ይሆናል፡፡ ቃላት ይደረደራሉ፤ ዐረፍተ ነገሮች ይሰካካሉ፤ ዐናቅጽ ይሰደራሉ እንጂ አእምሮን ያዝ ወይም ልብን ስልብ የሚያደርግ ፍሬ ነገር አይገኝበትም፡፡ በውስጡ ንጥረ ነገር የሌለው ሆድ የሚሞላ ምግብ እንደመብላት ነው፡፡ ሆድን ይሞላል እንጂ ለሰውነት ድጋፍ አይሆንም፡፡ ሰምተው ወይም አንብበው ሲጨርሱ የሚይዙት ነገር አይኖርም፡፡ ወፍጮ ቤት ደርሶ የመጣ ሰው ቢያንስ ጥቂት ዱቄት ሳይነካው እንደማይመጣ ሁሉ አንድን ነገር የሰማ ወይም ያነበበ ሰውም ጥቂት ነገር ሳያገኝ መቅረት የለበትም፡፡

ለሰው የሚገባው፣ ግልጽ የሆነና ፍሬ ያለው ነገር ለመናርና ለመጻፍ የቋንቋ ችሎታም ያስፈልጋል፡፡ ቡናን እንዲጠጣ የሚያደርገው ቡናነቱ ብቻ ሳይሆን አፈላሉና አቀዳዱም ጭምር ነው፡፡ ሳይሰክን የተቀዳ ቡናና መግለጫ ያጣ ሐሳብ አቅራቢ አንድ ናቸው፡፡ ሁለቱም የሚሰጡን ነገር እያላቸው አሰጣጡን አያውቁምና፡፡ የቋንቋ ችሎታ ማለት ጉዳዩን እስከ ጥግ ድረስ በመናገሪያው ቋንቋ አልቆ ለመናገር መቻል ነው፡፡ አልቆ ሲልም ይዘቱ በሚፈልገው ደረጃ ለማለት ነው፡፡ ጉዳዩን በምሳሌ፣ በዘይቤ፣ በከሳች ቃላትና ነገሩ እንዳይረሳ በሚያደርግ አገላለጥ ለማቅረብ መቻል፡፡ ሰሚና አንባቢ ሊገባው በሚችል መጠን እንዲረዳው ሆኖ ያልቀረበ ነገር ቃላትን መስማትና ማንበብ ብቻ ይሆናል፡፡ ወይም ደግሞ በአንድ ጠረጲዛ ላይ ምግቡን ሁሉ እንደ ተራራ ከምሮ እንደማቅረብ ያለ፡፡ ምንም እንኳን ምግቡ ጣፋጭና በባለሞያ የተሠራም ቢሆን ከክምር ውስጥ ምግብ እየጎረጎሩ ማውጣት ግን አማራጭ ላጣ ሰው ብቻ የሚሆን ነው፡፡ ያልረታን ንግግር የሚያዳምጠውና ያልበሰለን ጽሑፍም የሚያነበው አማራጭ ያጣው ሰው ብቻ ይሆናል፡፡
የሀገሬ ሰው ጎመን ብቻ መብላት ዐቅምም ጤናም እንደማይሰጥ ያውቃል፡፡ ለዚህም ነው ‹‹ሆድን በጎመን ቢደልሉት ጉልበት ዳገት ላይ ይለግማል›› የሚለው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ንግግር የሚያደርጉ ወይም የሚጽፉ ባለሥልጣናት፣ ምሁራን፣ ጸሐፍትና የእምነት መሪዎች ሰው የሚሰማቸው ወይም የሚያነባቸው አማራጭ ስለሌለው ነው ወይስ ገብቶት ነው? የሚለውን የሚለዩበት መንገድ ቢኖር መልካም ነበር፡፡ ‹‹እኛስ ይህቺን ክረምት ወጣናት በመላ
                                   በኩርማን እንጀራ ጎመን ተጠቅልላ› እንዲል ገበሬ፡፡ ሌላ አማራጭ አጥቶ ክረምቱን በጎመን ብቻ እንዳለፈው ሁሉ፣ ሰምቶን እየሄደ ያለው አማራጭ ከማጣት ሊሆን ይችላል፡፡ በተለይ ባለሞያዎችና ባለ ሥልጣናት ለንግግራቸውና ለጽሑፋቸው ተገቢውን የቅድሚያ ዝግጅት ማድረግ አለባቸው፡፡ እነርሱ ነገሮችን የሚጠሩበት ስያሜ ቃል (terminalogy) በኋላ የሚዲያው ትርክት ሆኖ ስለሚቀጥል እንዳመጣ መሰየምን ልማድ ማድረግ የለባቸውም፡፡ ያለበለዚያ ንግግራቸው ለሕዝቡ አዳቦል ይሆንበታል፡፡ አንገቱን እየነቀነቀ የማያደምጠው፡፡ ቢነቀንቅም ለትዝብት ያህል የሚነቀንቀው፡፡ መናገራቸው እንጂ ንግግራቸው የማያስታውሰው፡፡  
ሁለተኛው የአዳቦል መነሻ ደግሞ የማያውቁትን ወይም ያላመኑበትን ነገር ሊጽፉ ወይም ሊናገሩ ሲሞክሩ ነው፡፡ እንዲያውም በሀገራችን አንዳንድ ባለ ሥልጣናት እ- እ- እ- እያሉ አንጀት የሚጎትት ንግግር የሚናገሩበት ምክንያት፣ አንድም ያላመኑበትን ወይም የማያውቁትን አለያም ያልተረዱትን ነገር ሊናገሩ ስለሚፈልጉ ነው የሚል ምሳሌ ቀረበ፡፡ አንድን መረጃ አንብቦ ወይም ሰምቶ፣ ከዚያም ተረድቶ፣ በመጨረሻም ቅርጽ አስይዞ ለማውጣት የሚጠይቀው አእምሯዊ ሂደት አለ፡፡ በጉዳዩ ላይ ማሰብ፣ ለራስ መተንተን፣ በራስ ቋንቋ መረዳትና ለማቅረብ መቻልን ይጠይቃል፡፡ እህል ያገኘ ሁሉ ምግብ አይሠራም፣ ምግብ የሠራ ሁሉ ምግብ አያቀርብም፡፡ እህል ያገኘ ምግብ ለመሥራት፣ ምግብ ሠሪም ምግብ ለማቅረብ ሦስቱ ሞያዎች ያስፈልጉታል፡፡ እህሉን ማወቅ፣ ምግብ አሠራሩን ማወቅና ምግብ አቀራረቡን ማወቅ፡፡ ንግግርና ጽሑፍም እንዲሁ ነው፡፡ ጉዳዩን አስልቶ መስማት ወይም ማንበብ፤ አጥልቆ መረዳትና አሣምሮ ማቅረብን ይጠይቃል፡፡ 
አንዳንድ ጋዜጠኞቻችንና አሠልጣኞቻችን ከተለያዩ ምንጮች መረጃዎችን ወስደው  ሲያቀርቡ የሚያጋጥማቸው ችግር ከዚህ ይመነጫል አሉ ሊቃውንቱ፡፡ አንዳንዴ በሰላ ሁኔታ አይቃርሙትም፣ ወይም በሚገባ አይረዱትም፣ አለበለዚያ ደግሞ እንዴት ማቅረብ እንዳለባቸው አያስቡበትም፡፡ ምናልባት ያገኙት መረጃ አሳዝኗቸዋል፣ አስደስቷቸዋል፣ አስገርሟቸዋል፣ ወይም ደግሞ ከፕሮግራማቸው ጋር ሄዶላቸዋል፡፡ ነገር ግን በውስጣቸው አላመነዥኩትም፡፡ ጥሬውን እንደሆነ ነው ያስቀመጡት፡፡ እናውጣህ ሲሉት ቃል ያጥራቸዋል፡፡ እነርሱ ያገኙትን መረጃ ያህል ለኛ ማስተላለፍ ይከብዳቸዋል፡፡ ያኔ ነው ‹ቃላት ያጥሩኛል፣ ልዩ ነበር፣ ፐ፣ ጉድ ነው፣ አሪፍ ነው፣ ነፍስ ነው፣ የጸዳ ነው፣ አስደናቂ ነው› የሚሉ ነገሩን ከመግለጥ ይልቅ ስሜትን ብቻ የሚገልጡ ቃላት የሚበዙባቸው፡፡  አንዳንዴ ደግሞ ‹እንትን፣ ምን መሰለህ፣ ያ ነገር፣ እና፣› የሚሉ ቃላትን በመደጋገም መረጃ ሳይሰጡን ይቀራሉ፡፡ ወይም ደግሞ አንዱን ነገር ሰባት ጊዜ ይደጋግሙትና ያሰለቹናል፡፡  
ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ ዕውቀት አጠር ከመሆን የሚመጣ ነው፡፡ ስለምትናገረው ወይም ስለምትጽፈው ነገር በንባብ፣ በትምህርት፣ በልምድ ወይም በሌላ መንገድ የተገኘ የተከማቸ ዕውቀት ከሌለህ ያላስገባህውን ልታስወጣ አትችልምና ነገርህ ሁሉ አዳቦል ይሆናል፡፡ ከነጠፈች ላም ወተት እንደመጠበቅ ያለ፡፡ ስለ አንድ ነገር በልዩ ሁኔታ ያጠኑ፣ በዚያ መስክ የሠሩ ወይም ያነበቡና የሠለጠኑበት ሰዎች ይጻፉ ወይም ይናገሩ የሚባለው ወደ አእምሯቸው ባስገቡት መጠን ውኃ ያዘለ ነገር ሊያወጡ ስለሚችሉ ነው፡፡ ‹የምትናገረው ነገር ከሌለህ ዝም በማለት እርዳኝ› የሚባለው በዚህ ምክንያት ነው አሉ አንደኛው ሊቅ፡፡ ‹ከራበው በሬ ሥጋ አይጠበቅም› ይላሉ አፍሪካውያን› አሉ ሌላኛው፡፡ ዕውቀት ሲያጥርህ ንግግርህና ጽሑፍህ ትርጉም በሌላቸው ቃላት የታጀቡ ይሆናሉ፡፡ ከልክ በላይ የሆኑ አጎላማሾች ይታጨቁባቸዋል፡፡ ‹‹ከተማዋ በአንጸባራቂ ድል ታጅባ በፈጣን እድገት ላይ ትገኛለች› ዓይነት ይሆናል፡፡ ‹አንጸባራቂ› ና ‹ፈጣን› ምን ያህል ናቸው? እዚህ ውስጥ መጠኑን መለካት አትችልም፤ ሥራህ እንደ በቀቀን ማስተጋባት ብቻ ይሆናል፡፡ ሐሳቡን በራስህ መንገድ ማቅረብ ስለማትችል በአሰልቺ ቃላት(ጃርገን) ትሞላዋለህ፡፡  
አዳቦልነት በትምህርታችን፣ በንግግራችን፣ በዜናዎቻችን፣ በጽሑፎቻችንና በመግለጫዎቻችን ውስጥ እየበዛ በሄደ ቁጥር የመልዕክት ልውውጡ የተሰበረ፣ አንጆ አንጆ የሚል፣ ችክታ የበዛበት፤ ተግባቦት የሚያጥረውና ሐሳቡ የነጠፈ ይሆናል፡፡ ይኼ ደግሞ የዕውቀት ሽግግርን፣ የሐሳብ ምይይጥን፣ የመልእክት ዝውውርን ይጎዳል፡፡ ‹በተለይም ደግሞ ባለሥልጣናት፣ ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ የእምነት መሪዎች፣ የማኅበረሰብ መሪዎች፣ ጸሐፍት፣ የኪነ ጥበብ ባለሞያዎችና ሥልጠና ሰጭዎች በአዳቦል በሽታ እንዳይጠቁ ለዕውቀት፣ ለአቀራረብና ለምናቀርብበት ማኅበረሰብ ተገቢውን ቦታ መስጠት ይገባናል› ሲሉ ምሁራኑ ውይይቱን ዘግተውታል፡፡


ለረዥም ዓመታት በአንድ ሬዲዮ ጣቢያ የሠራ ጋዜጠኛ ለአንድ ጥናት ወደ ጣቢያው ይሄዳል፡፡ ከ30 ዓመታት በፊት እርሱ ራሱ ያደረገው ቃለ መጠይቅ ነበር፡፡ ቃለ መጠይቁ የተደረገላት ሴት አሁን በሕይወት የለቺም፡፡ ለዚህ ነበር እርሷ የሰጠቺውን ቃል ፍለጋ ወደ ሬዲዮ ጣቢያው የሄደው፡፡ ያገኘው ግን የጠበቀውን አልነበረም፡፡ የተቀዳው ቃለ መጠይቅ የለም፡፡ ምነው? አለ ጋዜጠኛው፡፡ ‹‹ብዙ ካሴቶችን እየደመሰስን ቀድተንባቸዋል፡፡ በዚያ ምክንያት ያንን ቃለ መጠይቅ አሁን አታገኘውም›› አሉት፡፡ እርሱም በዚህ አዝኖ ወጣ፡፡
ለነገሩ እርሱ በካሴቱ አዘነ እንጂ ከኢትዮጵያ ታሪክ መገለጫዎች አንዱ እየደመሰሱ መቅዳት ነው፡፡ የሚመጣ መንግሥት ወይም ባለሥልጣን፣ ዐዋቂ ወይም ታዋቂ፣ ታሪክ ጸሐፊ ወይም ዐቅድ ነዳፊ ከእርሱ በፊት ለነበረው ነገር ዋጋ ሰጥቶ፣ የየራሱን ሥራ ከመሥራትና የዘመኑን አሻራ ከማኖር ይልቅ ያለፈውን መደምሰስ ይቀናዋል፡፡ 

ሀገር የማታልቅ ሕንጻ ናት፡፡ መሠረቷ ዛሬ አልተጣለም፡፡ መሠረቷ ከተጣለ ቆየ፡፡ እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ድርሻ እየገነባ ይቀጥላል፡፡ የመጣው ሁሉ ባለው ላይ አዳብሮ፣ አሻሽሎ ወይም አሣምሮ የሚጨምር ከሆነ ሀገር እያደገች፣ እየበለጸገችም ትሄዳለች፡፡ የመጣው ትውልድ ሁሌም ከሥር ከመሠረቱ የሚያፈርሳት ከሆነ ግን ሀገር ባቢሎን ትሆናለች፡፡ ቅርስ እንጂ ሕይወት፣ ታሪክ እንጂ ዕድገት፣ ስም እንጂ ክብር አይኖራትም፡፡ ለጉብኝት እንጂ ለኑሮ አትሆንም፡፡ 
 ባቢሎን በታሪክ ቀድመው ከሠለጠኑ ሀገሮች ተርታ ነበረቺ፡፡ ነገር ግን የገዛት ሁሉ ከመሠረቷ እያፈረሰ እንደገና ሲሠራት፣ የመጣዉ ሁሉ እየደመሰሰ ሲቀዳባት ይሄው ዛሬም አላልፍላት ብሎ የጦር አውድማ ሆናለቺ፡፡ ስለ ኢራቅ ጥንታዊ ታሪክ የሚተረከውና የዛሬዋ ኢራቅ አይጣጣሙም፡፡ የመጡት ሁሉ በባቢሎን ካሴት ላይ እየደመሰሱ ሲቀዱ፣ መሠረት አልባ ጣራ ሊያቆመ ሲደክሙ፣ አሁን የመጡባት አሸባሪዎች ደግሞ ጨርሰው ታሪካዊ ቅርሶቿን በድጅኖ መናድ ጀመሩ፡፡ እየደመሰሱ መቅዳት ካንሰር መሆን ሲጀምር ይሄው ነው፡፡
ይኼ እፉኝታዊ ጠባይ ነው፡፡ እፉኝት የምትባል የእባብ ዘር አለች አሉ፡፡ አፈ ማኅፀኗ ጠባብ ነው፡፡ ከወንዱ ጋር ስትገናኝ የወንዱን አባለ ዘር ትቆርጠውና ወንዱ ይሞታል፡፡ ልጆቿን በማኅፀኗ ፈልፍላ ስትወልዳቸው ደግሞ ለመውጣት ስለማይችሉ ሆዷን እየቀደዱ እናታቸውን ገድለዋት ይወጣሉ፡፡ ልጆቹ ልጅ የሚሆኑት አባትና እናታቸውን ገድለው ነው፡፡ ያለፈውን ካልደመሰሱ መኖር አይችሉም፡፡
የመጣንበትንና የነበርንበትን ማንጠር ጠቢብነት ነው፡፡ መደምሰስ ግን እፉኝትነት፡፡ ማንጠር ማለት ደግሞ እንደ ቅቤ ነው፡፡ እናቶቻችን ቅቤ የሚያነጥሩት ለሁለት ነገር ነው፡፡ በአንድ በኩል ቅቤው ሲነጠር አንጉላው ተለይቶ ይቀራል፡፡ ቅቤውም ኮለል ብሎ ይወርዳል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቅመማ ቅመም በመጨመር በቅቤው ላይ ጣዕም ያክሉበታል፡፡ ወይም ቅቤውን ላቅ ወዳለ ሌላ የጣዕም ደረጃ ያሸጋግሩታል፡፡ ማንጠር ሲባል እንደዚሁ ነው፡፡ በታሪካችን፣ በባሕላችን፣ ወይም በልማዳችን ውስጥ እንደ አንጉላ ያሉ ነገሮች ተጨምረው ከሆነ በዕውቀትና ምርምር፣ በግልጽ ወይይትና ክርክር እሳት ላይ ጥዶ ማንጠር ነው፡፡ አንጉላውን ከለየን በኋላ ደግሞ በነበረው እሴታችን ላይ ሌላ እሴት መጨመር፡፡ 
ቅቤን ማንም አያነጥረውም፤ ባለሞያ ይጠይቃል፡፡ አንጉላውን የማስወገጃ መንገዱ ራሱ ልዩ ሞያ ጠያቂ ነው፡፡አንጉላ መስሎን ቅቤዉን ጭምር እንዳያስወግደው እንደ ዶሮ ላባ ባለ ስስ ነገር እየለዩ ማንጠርን ይጠይቃል፡፡
ታሪካችንንና ባሕላችንን፣ ወጋችንንና ልማዳችንን ስንመረምርና አንጉላውን ስንለይ፣ እንደ ቅቤ አንጣሪው በሞያ መሆን አለበት፡፡ ስሜት ቦታ ሊያገኝ አይገባም፡፡ ቅቤ አንጣሪ ስሜት ውስጥ ከገባ ምች ይመታዋልና፡፡ አረሙን እንነቅላለን ብለን ስንዴውን ጨምረን እንዳንነቅለው ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፡፡ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ፍጆታ ብለን የምንሠራቸው ሥራዎች አዙሪት ውስጥ እንዳይጥሉን ጉዳዩን የሞያና የዕውቀት ጉዳይ ማድረግ ይገባናል፡፡ ‹ዕውቀት አጠር፣ ስሜት መር› ከሆነው ጉዟችን ይልቅ ‹ዕውቀት መር፣ ስሜት አጠር› ወደሆነው ሥልጣኔ ካልወጣን በስተቀር እዚያው ጨለማው ውስጥ ስንኳትን እንኖራለን፡፡ 
ቅቤ አንጣሪ ሰው ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ያስፈልገዋል፡፡ ምች እንዳይመታው፡፡ የቅቤ ምች ያጠናግራል ይባላል፡፡ ቅቤውን በጥንቃቄ ያነጠረቺ ባለሞያ ናት ‹‹ቅቤ አንጣሪዋ እያለቺ ጎመን ቀንጣሿን ምች መታት› ብላ የተሳለቀቺው፡፡ ነባሩን ነገራችንን ስናነጥር ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ወሳኝ ነው፡፡ የዘመን ምች መትቶ እንዳያጠናግረን፡፡ ጎጠኛነት፣ የፖለቲካ ፍጆታ፣ የሥልጣን ፍቅርና ጊዜያዊ ጥቅም የሚባሉ ምቾች አደገኞች ናቸው፡፡ እነዚህ ምቾች የመቱት ሰው ቅቤውን በሚገባ ማንጠር ቀርቶ ሌላ በሽታ በራሱ ላይ ይጨምራል፡፡ ጤነኛ የነበረው አንጣሪ ተጣሞ፣ ዓይኑ ጠፍቶ፣ ፊቱ ቆሳስሎ ይወጣል፡፡ ከዚያ በኋላ እርሱ ያለፈው ታሪኩን ሁሉ የሚያየው በማንጠሪያ ዓይኑ ሳይሆን በተጠናገረ ዓይኑ ነው፡፡ 
አሁን በደምስሶ መቅዳት ሥራ ላይ የተሠማሩት ብዙዎቹ ወገኖቻችን ምች የመታቸው ናቸው፡፡ ዓይነ ልቡናቸውን ምች ስለ መታው ቅቤውንና አንጉላውን መለየት አልቻሉም፡፡ አንጉላ መስሏቸው ሁሉንም ነባር ቅቤ ሊያስወግዱ የቋመጡ ናቸው፡፡ የዛሬውን መንግሥተ ሰማያት ለማሰኘት የትናንቱን ሲዖል ማድረግ፣ የእነርሱን ዘመን የተድላ ዘመን ለማድረግ አላፊውን ዘመን የመከራ ዘመን ማድረግ፣ የአሁኑን አስተሳሰባቸውን ዘመናዊ ለማድረግ ያለፈውን ሁሉ ኋላ ቀር ማሰኘት የግድ ይመስላቸዋል፡፡ ያለፈው የተቀዳበትን ካሴት አዳምጠው ቀጥሎ የራሳቸውን ከመቅዳት ወይም አዲስ ካሴት ከመጠቀም ይልቅ ደምስሰው ካልቀዱ አይረኩም፡፡ አዲስ ሲሠሩ ከሚደሰቱት በላይ ነባሩን ሲያጠፉ የሠለጠኑ ይመስላቸዋል፡፡
ሰው በአንድ ቦታ ስለተሰበሰበ ብቻ ሀገር አይሆንም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ እሥራኤላውያን አሜሪካና ፖላንድ መኖር ይበቃቸው ነበር፤ ለፍልስጤማውያንም ዮርዳኖስና ሊባኖስ የሚኖሩት የካምፕ ኑሮ በቂ ነበር፡፡  ሰፊ መሬት ብቻውንም ሀገርን አይመሠርትም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ አንታርክቲካ ሀገር ይሆን ነበር፡፡ ሀገር ግን ከሰውም ከመሬትም በላይ ናት፡፡ ሰው በመሬቱ ላይ ሲኖር የሠራው ታሪክ፣ ያካበተው ባሕል፣ የደነገገው ወግና ሥርዓት፣ ያዳበረው ቋንቋ፣ ያመጣው ለውጥ፣ የፈጠረው ዘዴ፣ የገነባው ሥነ ልቡና፣ የተከተለው እምነት፣ የእርስ በርሱ መስተጋብር፣ ዓለምን የሚያይበት ርእዮተ ዓለም፣ ሥነ ቃሉ፣ ሌላም፣ ሌላም፣ ሌላም ተዋሕደው የሚፈጥሩት ነገር ነው – ሀገር፡፡ 
 
እነዚህን የተሠራንባቸውን ነገሮች ነው ማንጠር የሚያስፈልገው፡፡ መጀመሪያ እንሰብስባቸው፣ እንመዝግባቸው፣ እንለያቸው፣እንዘግባቸው፣ እንቀርሳቸው፣ እንወቃቸው፡፡ ከዚያ እናጥናቸው፣ እንመርምራቸው፡፡ በመጨረሻም እናንጥራቸው፡፡ ገመዱ ውስብስብ ነው፡፡ ለዘመናት የተፈተለና የተገመደ፡፡ ርጋታ፣ ትዕግሥትና ጥበብ ይጠይቃል፡፡ ወስነን አይደለም ማወቅ ያለብን ዐውቀን ነው መወሰን እንጂ፡፡ አንዳንዴ መጀመሪያ እንወስናለን፣ ከዚያ እንሰይማለን፣ ቀጥለንም እንፈርጃለን፣ በመጨረሻም እንመታለን፡፡ በዚህ ሁሉ ሂደት ውስጥ ግን ዕውቀት፣ ጥናትና ማንጠር ቦታ አይሰጣቸውም፡፡ እንዴው ዝም ብሎ ‹ስቅሎ ስቅሎ› ነው፡፡ ‹ትዕዛዝ ከበላይ፣ እግር ወደላይ› ይሆናል መመሪያው፡፡
 
በዚህ መንገድ ስንቱን እየደመሰስን ቀዳን፡፡ ስንቱን ነባር ዕውቀት ሳንጠቀምበት እንደ ገናሌ ወንዝ ፈስሶ ፈስሶ ቀረ፡፡ ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል የተባለው በራሳችን ላይ ደርሶ ብልሆቹ አውሮፓውያን የራሳችንን መጻሕፍት ሰብስበው፣ ባሕላችንን አጥንተው፣ ታሪካችንን ፈትሸው፣ ነባር ዕውቀቶችን መርምረው – በውስጣቸው ያገኙትን ጥበብ ለዘመናዊ ሥልጣኔያቸው ተጠቀሙባቸው፡፡ እኛ ግን እየደመሰስን ስንቀዳ፣ አንድም ትናንት ሳይኖረን ዛሬን እናቆማለን ብለን መከራ እናያለን፡፡ በጣም የሚገርመው ግን እኛ የትናንቱን ደምስሰን እየቀዳን፣ የነገዎቹ የኛን አይደመስሱም ብለን ማመናችን ነው፡፡ ይኼንኑ አሠራር አይደል እንዴ የምናቆያቸው፡፡   

በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ
የሐዲስ ዓለማየሁ የባሕል ማዕከል 3ኛ ጉባኤ ላይ የቀረበ
‹‹አበሻ ባል ሚስቱ ስታረግዝ እርሱ ዕንቅልፍ አይወስደውም›› ይባላል፡፡ ስለምን ቢሉ የልጅ ስም ፍለጋ፡፡ ስም ደግሞ በአበሻ ምድር እንዲሁ አይወጣም፡፡ ቢቻል ከአያት፣ ካልተቻለም ከአባት ጋር የሚገጥም፣ ዘመኑንና ሁኔታውን የሚያሳይ፣ ተስፋንና  ምኞትን የሚያመለክት፣ አንዳንዴም ድጋፍንና ተቃውሞን የሚገልጥ መሆን አለበት፡፡ ‹ጅል እንደ ሠራው በርና መቃን የማይገጥም ስም ይዘህ. ይባላልኮ፡፡ በተለይ በሰሜኑ ማኅረሰብ ስም መጠሪያ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ መዝገብ ታሪክን፣ እንደ ሚዲያ ሐሳብን፣ እንደ መጽሐፍ ፍልስፍናን፣ እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት እምነትን፣ እንደ ሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞን የሚያሳይ  የመገናኛ መሣሪያ ጭምር ነው፡፡

በደርግ ዘመን ተቆራጭና መዋጮ በዝቶ ሠራተኛውን መከራ ሲያሳየው፣ በባሕርዳር ጥጥ ፋብሪካ የነበረ በዛብህ የተባለ ወዛደር ለሁለት ልጆቹ ‹ተቆራጩ› እና ‹መዋጮው› የሚል ስም አወጣላቸው፡፡ የልጅ እናቱ በየአሥራ አምስት ቀኑ የልጆቿን ተቆራጭ ልትወስድ ስትመጣ ደመወዝ ከፋዩ ድምፁን ከፍ አድርጎ ‹ተቆራጩ በዛብህ› ‹መዋጮው በዛብህ› እያለ የሕዝቡን ተቃውሞ ሲገልጥ ኖሯል፡፡ በአብዮቱ ዘመን የተወለዱ ብዙ ልጆች ‹አብዮት› የሚለውን ስም በመያዝ ታሪክ መዝግበው አልፈዋል፡፡ ኀዘንን ለመርሳት ያስችላል የተባለውን ልጅ  ማስረሻ፣ ከመከራ በኋላ የተወለደውን አልፈነው፣ አልወልድም ካሉ በኋላ የተወለደውን እምቢ በል፣ ከሌላ ተረገዘ ተብሎ ሲታማ አባቱን መስሎ የተወለደውን ምስክር እያሉ መጥራት ከስም በላይ ጉዳይ ያለበት ነው፡፡ ከዐሠርት ዓመታት በፊትም ልጃቸው ‹ይገደብ ዓባይ› ብለው ትንቢት የተናገሩ ወላጆችም ነበሩ፡፡
እንኳን የልጅ ስም የውሻ ስም ከአንድ ጋዜጣ በላይ የሆነ ማኅበራዊ ጉዳይን ሲገልጥ ኖሯል፡፡
ሁለት ውሾች አሉኝ የማሳድጋቸው
አንዱ ሰምቶ መቻል ሌላው መተው ናቸው
የሚለው ሐሳብኮ ባለስሞቹ ውሾች ሊሸከሙት የሚከብዳቸው ነው፡፡ 
በጎንደር ከተማ በ1970ዎቹ መጀመሪያ የነበሩ አቶ ጨከነ የተባሉ አባት ለመጀመሪያዎቹ ሁለት ልጆቻቸው መንግሥቱና መልአኩ የሚል ስም አወጡ፡፡ ልጆቹም ‹መንግሥቱ ጨከነ› ‹መልአኩ ጨከነ› ተባሉ፡፡ ‹የእግዜር ታናሽ ወንድም› የተባለለት መልአኩ ተፈራ ሰምቶ ሊገላቸው ቢነሣ አገር ጥለው ጠፉ፡፡ ጠፍተውም ዝም አላሉም፡፡ የመከራው ዘመን ሲረዝም በፈጣሪም ተስፋ ቆረጡ መሰል ሦስተኛ ልጃቸውን ‹አምላኩ ጨከነ› ብለው ስም አወጡለት፡፡ 
እኒህ ዛሬ የምንዘክራቸው ሐዲስ ዓለማየሁ እንደሚተርኩልን በአንድ ወቅት እዚህ ምሥራቅ ጎጃም ሲመጡ ‹ኦክስጅን› የሚባል ስም ይሰማሉ፡፡ ገርሟቸው አባትዬውን ሲጠይቁት ትርጉሙን አያውቀውም፡፡ ‹ታድያ እንዴት አወጣህለት› ሲሉት ‹‹በአንድ ወቅት ደጃዝማች ግርማቸው ተክለ ሐዋርያት እዚያ አካባቢ መጥተው ይህንን ቃል ሲሉት ሰማኋቸው፡፡ መቼም ከእርሳቸው አፍ ክፉ አይወጣም ብዬ ኦክስጅን አልኩት› ብሎ መለሰላቸው፡፡ 
እኛ አገር ስም ብዙ ነገር ነው፡፡
እንዲያውም ሰሞኑን አዲስ አበባ አንድ ስም ሰማሁ፡፡ ቆጥቡ፣ አስቀምጡ በሚባልበት ዘመን የተወለደች ስለሆነች መሰለኝ፤ ‹ባንኬ› ብለው ነው የሰየሟት፡፡ እነ ገንዘቤ፣ ንብረቴ፣ ሀብቴ አንድ ደረጃ አድገው ‹ባንኬ› ሆኑ ማለት ነው፡፡ ምነው ብዬ ብጠይቅ ሰውዬው ለ20/80ም ይሆን 40/60 የሚቆጥቡት ብር አጠራቸው፡፡ ደግሞ ጓደኞቻቸውና ዘመዶቻቸው ይህን ያህል ብር ቆጠብን ሲሉ ይሰማሉ፡፡ ስማቸው መልአኩ ነበርና ልጃቸው ‹ባንኬ መልአኩ› ብለው የኔስ ባንክ መልአኩ ነው ብለው ተጽናኑ አሉ፡፡ ደቡብ ወርጄ ደግሞ ‹መቶ ሃያ› የሚባል ስም ሰምቼ ነበር፡፡ መቼም በ120ው የጌታ ቤተሰብ ሰይመውት ነው ስል ለካስ ነገሩ ሌላ ነው፡፡ ‹‹በቴሌቭዥን 120 ፕሮግራም ሲጀመር ስለተወለደ ነው›› አሉኝ፡፡ 

ከታምሩ መቅድሙ እንዳይበዛ ብለን አሁን ተአምሩን መንገር እንጀምራለን፡፡
የሐዲስም አባት እንዲሁ የሆኑ መሰለኝ፡፡ ወላጆቻቸው ‹ዓለም አየሁ› ብለው ስም ሲያወጡላቸው አንዳች ተስፋ ነገር መሰነቃቸውን ያሳብቅባቸዋል፡፡ ለነገሩ ያ ዘመን  የተስፋ ዘመን ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በቴዎድሮስ የጀመረችውን ዝመና በምኒሊክ በኩል እውን እያደረገች የነበረችበት ዘመን፡፡ መኪና፣ ስልክ፣ ፖስታ፣ ዘመናዊ ትምህርት ቤት፣ የቧንቧ ውኃ፣ አዲስ ሆነው እየመጡ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ወደ አዲስ ሥልጣኔ እየገሠገሠች የነበረችበት ዘመን፡፡ ይኼን ዘመን ለታሪክ ካስቀሩልን መዛግብት መካከል የዚያ ዘመን ስሞች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ እንደ ሐዲስ ዓለማየሁ አያት ያሉ ተስፋ ሰናቂዎች ‹ዓለም አየሁ› ብለው በልጆቻቸው ስም ዘክረውታል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ልጅ እምቢ ብሏቸው፣ እንደ ሐናና ኢያቄም፣ ወይም እንደ እግዚእ ኀረያ እና ጸጋ ዘአብ ሲናቁና ሲተቹ ኖረው የጀግና ልጅ አባት የሚሆኑ ጀግና ሲያገኙ ጊዜ ‹ዓለም አየሁ› ብለዋቸው ይሆናል፡፡ በኛ ትውፊታዊ ትርጉም ‹ዓለም› ብዙ ነገር ነዋ፡፡ ዓለም – ተድላ ነው፣ ተስፋ ነው፣ ኑሮ ነው፣ ሀብት ነው፣ ትዳር ነው፡፡
‹ዓለምሽ ዛሬ ነው ዛሬ
እህህ እቴ ሸንኮሬ›› እንዲል፡፡ 
ዓለምን መቅጨት፣ ዓለምን ማየት፣ ከዚህ ግጥም ጋር ለምስክርነት ተቆጥረዋል፡፡ ‹ዓለሜ› ሲል ደግሞ ሁለመናዬ የሚለውን ይተረጉም ዘንድ አለው፡፡ ‹‹የዓለም የሲሳይ ቤት ይሁን› ሲባልም ትርጉሙ ሁለመና ነው፡፡ የማይተነተን፡፡ በርግጥ የዛሬ ተጋቢዎች ‹‹እኔ በመሠረትኩት ትዳር፣ እኔ በሠራሁት ቤት – ዓለምና ሲሳይ ምን አገባቸውና የእነርሱ ቤት ይሆናል› ብለው ይሞግታሉ አሉ፡፡
ታድያ ተስፋ ተስፋን ወለደና አቶ ዓለም አየሁም ልጃቸውን ‹ሐዲስ› ብለው ጠሩት፡፡ አዲስ ዘመን፣ አዲስ ዓለም፣ አዲስ አበባ የሚባሉ ተስፋን የሰነቁ ስሞች በወጡበት ዘመን፡፡ የመታደስ፣ የመነሣት፣ የመሠልጠን፣ እንደ አዲስ የመጀመር ምኞት ሥግው በሆነበት ኢትዮጵያዊ ጊዜ ነበርና፣ እርሳቸውም ‹ሐዲስ ዓለም አየሁ› ብለው ትንቢት መሰል ስም ሰጡ መሰለኝ፡፡ 
ታድያ ለእኔ ፍቅር እስከ መቃብርን የደረሱት ልጅዬው ሐዲስ ሳይሆኑ አባትዬው አቶ ዓለም አየሁ ይመስሉኛል፡፡ ቢያንስ እርሳቸው ረቂቁን አውጥተው፣ ትልሙን ተልመው፣ ቅመሙን ቀምመው ለሐዲስ ሳይሰጡ አልቀሩም፡፡ እንገር ሲያጠጧቸው፣ ቅቤ ሲያውጧቸው፡፡ ፍቅር እስከ መቃብርና ሌሎቹም የሐዲስ ዓለም አየሁ ድርሰቶች – አዲስ ዓለም አየሁ ናቸው፡፡ 
በፍቅር እስከ መቃብር ውስጥ ፊውዳሊዝም እየበሰበሰ፣ ሊሸከሙት ከሚቻለው በላይ እየሆነ ይታያል- በዚያ ውስጥ ጉዱ ካሣ – አዲስ ዓለም አየሁ ይላል፡፡ በድንጋይ ካብ እየመሰለ ሲፈርስ ይታየዋል፡፡ እንደ ሰብለና በዛብህ ያሉ አዳዲስ ትውልዶች፣ ቀደምቱ በቀረጸላቸው ፊደል ብቻ የማይጽፉ፣ ነባሩ በቀደደላቸው ቦይ ብቻ የማይፈሱ፣ የሚያፈተልኩ አዲስ ዓለመኞች ይታያሉ፡፡ ከፊውዳሉ ማኅጸን ውስጥ እንደ ጉዱ ካሣ ያሉ ፈንቅሎች፣ አይፈሬዎችና ለውጥ ፈላጊዎች እንደሚመነጩ – ሐዲስ ዓለም – አይተዋል፡፡ አንድ ሥርዓት እየበሰበሰ፣ ከሕዝቡ የልቡና ሸክም በላይ ሲሆን ያወጣቸው ሕጎችና አሠራሮች እንኳን ሊታደጉት እንደማይችሉ- በፊታውራሪ መሸሻ የደብረ ማርቆስ ክስና ፍርድ – አዲስ ዓለም አሳይተዋል፡፡ 
በነ አበጀ በለው ዐመጽ በኩል አይቀሬ የነበረውን የገበሬዎች እምቢ ባይነት አባታቸው ቀድመው ቢያዩት መስሎኝ – ልጃቸውን – ገና ምኑም ሳይወጠወጥ ስማቸው – ‹ሐዲስ ዓለም አየሁ› ያሏቸው፡፡ 
ደግሞም ‹ሐዲስ› ነገር ሁሉ ደግ አይደለምና የዚህች ሀገር ‹ክፉው› ሐዲስም ታይቷቸው ነበር አባትዬው፡፡ እንደነ አባ ሞገሴ ያሉ በሞራል የወረዱ፣ ተልዕኳቸውንም የሳቱ፣ ሥልጣን የያዘውን ብቻ ማወደስ ሥራቸው የሆነ መንፈሳዊ መሪዎች፣ በነ አቡነ ጴጥሮስ ቦታ እንደሚተኩ ታይቷቸዋል ልበል፡፡ በ65 – 66 ብቅ ያለው የእንቡጦቹ የአብዮት ሙሽሮች የወጣቶቹ የለውጥ ጉዞ፣ ከስኬት ሳይደርስ መንገድ እንደሚቀር ቢታያቸው አይደል እንዴ – ሰብለ ወንጌልንና በዛብህን ጎሐ ጽዮን ላይ ያስቀሯቸው፡፡ እንደነ በዓሉ ግርማ፣ እንደነ አቤ ጎበኛ፣ እንደነ ግርማቸው ተክለ ሐዋርያት ያሉ ጉዱ ካሣዎች፣ እዚህች ሀገር ፍጻሜያቸው ለውጥ አምጥተው፣ በትውልዱ ዘንድ ከፍ ብለው መታየት ሳይሆን፣ ከለውጥ አምጭው ትውልድ ጋር አብሮ መሞትና መቀበር መሆኑን ቀድመው በትንቢት መነጽር ቢያዩም አይደል እንዴ ጉዱ ካሣን ከነ ሰብለና በዛብህ ጋር ጎሐ ጽዮን የቀበሩት፡፡ 
በዛብህ አዲስ አበባ ሩፋኤል ነበር የመጣው፡፡ ሰብለንም ሊያመጣት ያሰበው አዲስ አበባ ሩፋኤል ነበር፡፡ ሩፋኤል ደግሞ ፈታሔ ማኅፀን ነው፡፡ የጦቢትን ዓይንም የገለጠ እርሱ ነው፡፡ ‹‹በዓለ መድኃኒትም›› ይባላል፡፡ በዛብህ ግን ማኅፀን ፈቺውንና በዓለ መድኃኒቱን አየው እንጂ አላገኘውም፣ ተሳለመው እንጂ አልተሾመበትም፡፡ ይህቺ ሀገር አንዱ የሚያስፈልጋትኮ የኪነ ጥበብ፣ የኢኮኖሚ፣ የዲፕሎማሲ፣ የዕውቀት፣ የጥበብ፣ የፖለቲካ፣ የለውጥ፣ የሰብአዊነትና የእምነት ጀግኖች ትወልድ ዘንድ ፈታሔ ማኅፀን ነው፡፡ የሚያዋልድ፣ ከምጥ የሚያሳርፍ፡፡ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ አካባቢያዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ ዕውቀታዊ፣ ተቋማዊ ሕመሞቿ እንዲድኑ በዓለ መድኃኒት ያስፈልጋታል፡፡ የትውልዱም ዓይን ከጫትና ከሐሺሽ፣ ከፊልምና ዳንስ፣ ከውጭ ሀገርና ከስደት፣ ላቅ ያለ ነገር እንዲያይ እንደ ጦቢት ዓይን ገላጭ ያሻታል፡፡ በዛብሃዊው ሰብላዊውና  ጉዱ ካሣዊው ትውልድ ግን ገና አላገኘውም፡፡ ጎሐ ጽዮን ላይ ቀረ፡፡ ይህን ይሆን አባትዬው ‹ሐዲስ ዓለማየሁ› ያሉት፡፡ ‹በሩቅ አይቶ የሚሳለም ግን የማያገኝ› ትውልድ የሚኖርባትን ኢትዮጵያ አይተው፡፡  
ጎሐ ጽዮን – ጽዮን ኢትዮጵያ አይደለችም እንዴ፡፡ የጽዮን ሀገር ናትና ኢትዮጵያ፡፡ ‹‹በስመ ኀዳሪ ይፄውእ ማኅደር – እንዲል በአዳሪዋ በጽዮን ስም ማደሪያዋ ኢትዮጵያም ጽዮን ተብላ ተጠርታለች፡፡ – የጽዮን ጎሕ – እዚያ ነው አዳዲስ ለውጠኞች የተቀበሩት፡፡ አብዮት ልጇን ትበላለች እንዲል መሆኑ ነው፡፡ ብዙዎቹ በዛብሆችና ሰብለዎች፣ ብሎም ጉዱ ካሣዎች – የጽዮን ጎሕ ውስጥ ነው የተቀበሩት፡፡ ዓባይ በረሃ ሳይወስደቸው፤ ግን ሳይሻገሩት፣ አፋፍ እያስቀራቸው፡፡ የጽዮን ጎሕ ውስጥ ገብተው ቀሩ፡፡ ችግሩ ደግሞ ደጀንና ጎሐ ጽዮን ከመለያየታቸው ላይ ነው፡፡ ደጀን ማዶ ጎሐ ጽዮን ማዶ፤ በመሐል በረሃ፡፡ ደጀኑ ሕዝብ ጎሑን አይከተል፣ ወይ ጎሑ ደጀኑን አያስከትል፡፡ ጎሕና ደጀን ለየብቻቸው ይሄዱና ደጀኑ ለውጥ አምጭዎችን ጎሐ ጽዮን ላይ ቀብሮ ዝም ይላል፡፡ ይህን ነው ያዩት – ዓለም አየሁ፡፡
ራሳቸው ሐዲስስ ቢሆኑ ይህንን ዐርባ ዓመት የተቀመጠ የጎጃም ጠላ የመሰለ ልዩ ድርሰት እንዳልደረሱ ተቆጥረው ባለፉት ዘመናት ጎሐ ጽዮን ላይ ተቀብረው አልነበር እድሜያቸውን የጨረሱት፡፡ አባትዬው የጻፉትን ድርሰት ልጅዬው ፊልሙን በቁም አልሠሩትም እንዴ፡፡    
ምርቅና ፍትፍት፣ ግርድና ምርት፣ ጥሬና ብስል የሚጋፉባትን፤ ደጀንና ጎሐ ጽዮን የተለያዩባትን – አዲሷን ኢትዮጵያ አይተው ነው- ሐዲስ ብለው የሰየሟቸው፡፡ እስመ ስሙ ይመርሖ ኀበ ግብሩ እንዲል፡፡ 
 

ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ሲመኙት የኖረ፣ የትውልድን ሕልም እውን ያደረገ፣ በዘመናዊ ታሪካችን ውስጥ ሊጠቀስ የሚችል የዚህ ትውልድ ሥራ ነው፡፡ ‹ዓባይን መገደብ› ታላቅ ሐሳብ፣ ታላቅም ውሳኔ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከአካባቢው ሀገራት ጋር የምታደርገውን ውይይት ቋንቋውን የቀየረ፣ የግዮን ምንጩ ከኢትዮጵያ ተራሮች መሆኑን ከብራና አውርዶ መሬት ላይ የጻፈ ነው፡፡ 
 
ስለ ሕዳሴው ግድብ የሚሠሩት ማስታወቂያዎች ግን ፈጽሞ ግድቡን የማይመጥኑ፣ እንኳን ለዓባይ ግድብ ለኛ ቤት አጥርም የማይሆኑ፣ በውስጣቸው ምንም ዓይነት ሀገራዊ ርእይና ፍልስፍና የሌለባቸው፤ ከጠላና እንጀራ የማያልፉ ናቸው፡፡ እንዴው ግድቡ አፍ ስለሌለው እንጂ በስም ማጥፋትና በክብረ ነክ ወንጀል ይከስ ነበር፡፡  የታሪክ ባለሞያዎች፣ የፖለቲካ ጠበብት፣ የኪነ ጥበብ ልሂቃን፣ የእምነትና የባሕል ምሁራን፣ የሥነ ቃል አጥኒዎች፣ የሐሳብ መሪዎችና የሕዳሴ ኮከቦች መነጋገሪያ፣ መከራከሪያ፣ ሐሳብ ማራቀቂያ፣ ትውልድ መቅረጫ፣ ትውልድ ማነሣሻ፣ መሆን የነበረበት የሕዳሴው ግድብ የቀልደኞች ማቧለቻ ሲሆን እንደማየት ያለ የክፍለ ዘመኑ ርግማን የለም፡፡

እኔ እንዲያውም እነዚህ ግድቡን የማይመጥኑ ማስታወቂያዎች በግብጽ ነው እንዴ ስፖንሰር የሚደረጉት? እላለሁ፡፡ ግድቡኮ የግንባታ ሂደት ጉዳይ ነው፡፡ መንግሥት ከአንድ ኮንትራክተር ጋር ተነጋግሮ የሚያጠናቅቀው፡፡ ዋናው ጉዳይ አስተሳሰቡ ነው፡፡ ለምን እንገነባዋለን? የምን ማሳያ ነው? ዓባይን እንገድባለን ስንል ምን ማለታችን ነው? ዓባይ በኢትዮጵያ እምነት፣ ታሪክ፣ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ባሕል ውስጥ ምን ቦታ ነበረው? አሁን ወደየትኛው ቦታ እየወሰድነው ነው? ዓባይን የመገደብ ሂደትና ስኬት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ መፍጠሪያ መስፈንጠሪያ እንዲሆን ምን እንድርግ? እነዚህን ነው መተንተን፣ እነዚህን ነው መሥራት፣ እነዚህን ነው የሕዝብ ገንዘቦች ማድረግ፣ በእነዚህ ላይ ነው መግባባት ያለብን፡፡ ግድቡ መሠራት ያለበት በዜጎች ላይ ቀልደን ሳይሆን ዜጎችን በብቃት አሳምነን ነው፡፡  
 
ግድቡ ያልቃል፡፡ ወንዙም ይቀጥላል፡፡ የሚቀረው ታሪክና ሐሳቡ ነው፡፡ አሜሪካውያን በአሪዞናና በኔቫዳ መካከል የሚገኘውን የሁቨር ግድብን የሠሩት(እኤአ ከ1931-36) በችግር ወቅት ነው፡፡ ገንዘባቸው፣ ጉልበታቸውንና ዕውቀታቸው ሠውተው ነው የሠሩት፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ገንቢዎች ሕይወታቸው ከፍለውለታል፡፡ አያሌ አሜሪካውያን ዛሬ ግድቡን ለመጎብኘት ሲሄዱ ከግድቡ በላይ ስለ ግድቡ አሠራር የሚያሳየውን ሙዝየም መጎብኘት ነው የሚያስደስታቸው፡፡ ለምን ተገነባ? የዚያን ዘመን መሪዎችና ሕዝብ ምን ነበር ዓላማቸው? እንዴት ነበር የገነቡት? እነማን ምን ዓይነት መሥዋዕትነት ከፈሉ? ግድቡን ሲገደቡ አሜሪካን የት ማድረስ ነበር ሕልማቸው? ይህን ነው ሙዝየሙ የሚተርከው፡፡ የተሠው ዜጎችን፣ የቀን ራሽን እየተሰጣቸው የገነቡ አሜሪካውያንን፣ በአነስተኛ ክፍያ ለሀገራቸው የሠሩ ባለሞያዎችን ያሳያል ሙዝየሙ፡፡
 
ሁቨር ግድብ ለአሜሪካውያን ግድብ ብቻ አይደለም፡፡ የአልሸነፍ ባይነት መገለጫ፣ ሀገርን ከግል ጥቅምና ከጊዜያዊ ችግር በላይ አድርጎ ማሰቢያ፣ ብንወድቅ እንነሣለን፤ ‹ኢኮኖሚያችን ለጊዜው ቢወድቅም፣ እኛ ሕዝቦች ግን አልወደቅንም› የሚለውን የአሜሪካውያንን የዚያ ዘመን ፍልስፍና ማረጋገጫ ነው፡፡ ጽናታቸውንና የሀገር ፍቅራቸውን ማሳያ ነው፡፡ አስጎብኝዎቹ እንደሚሉትም ‹እንደ ሕዝብ አንወድቅም› የሚለውን ፍልስፍናቸው ማስመስከሪያ ነው፡፡ 
 
የሕዳሴው ግድብ ግን ‹የዚህ መሥሪያ ቤት ሠራተኞች ጎበኙት› ከሚለው ዜና በዘለለ ‹ስለምኑ› የማይወራለት፣ ፍልስፍናው የማይተነተንለት፣ ከግድቡ በላይ፣ ከአሸዋው፣ ከሲሚንቶውና ከብረቱ በላይ፤ ከጠጠሩና ከድንጋዩ ባሻገር ግድቡ ምንድን ነው? የሚለውን መግፍኤ ሐሳብ የሚናገርለት ያጣ ምስኪን ግድብ ነው፡፡ ልጆቻችን ነገ ግድቡን አይደለም የሚጎበኙት፡፡ እንዴት ተሠራ፣ ለምን ታሰበ፣ አባቶቻችን ምን ለውጥ ነበር ሊያመጡ ያሰቡት? የነበሩትን ተግዳሮቶች እንዴት አለፏቸው? የግድቡ መሠራትስ ምን የአስተሳሰብ፣ የአሠራር፣ የኢኮኖሚ፣ የባሕል፣ የዲፕሎማሲና የሀገር ገጽታ ለውጥ አመጣ? የሚለውን መመርመር ነው የሚፈልጉት፡፡ ከግድቡ ጀርባ የነበረውን የኢትዮጵያውያን ፍልስፍናና መንፈስ ነው የሚሹት፡፡  
 
ያ ሁሉ ቀረና፣ ጽድቁ ቀርቶ በወጉ እንኳን የሚኮንነው በማጣት …
 
ጭራሽ ሰሞኑን የምናያቸው ማስታወቂያዎች ደግሞ የግድቡን ሐሳብ አውርደው አውርደው ገንቦ ጠላና የብረት ምጣድ ጥብስ ላይ የሚጥሉ ሆኑ፡፡ ከዚህ በፊት ከጉንጭ የተረፈ ዳቦ በመብላት፣ በጎልማሶች ትምህርት ላይ በማሾፍ የተሠራውን ማስታወቂያ ስንታገሠው አሁን  ደግሞ  ‹ሕዳሴው ወርዶ ወርዶ› የጠላና የጥብስ መጨዋቻ ሆነ፡፡ ፀጉሯ እንኳን ወርዶ ወርዶ ‹ይጠቀለላል እንደ ሰርዶ› ነበር የተባለው፡፡ እንዴው ከዚህ የተሻለ ከፍ ያለ ሐሳብና የመንገሪያ መንገድ አጥተን ነው የግድቡን ሐሳብ በጋን ጠላና በብረት ምጣድ ጥብስ የምናሰቃየው? 
 
አሁን የሦስት ብር የስልክ ሎተሪን ለመግለጥ ‹መቼ ነው መብላት የሚጀመረው?›› ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል? መብላት ከተጀመረ ቆየ አይደለም እንዴ? መብላቱ አስቸግሮ አይደል እንዴ ፀረ ሙስና የሚባል መሥሪያ ቤት የተቋቋመው? አሁንኮ ሰው  መብላትንና መበላትን ለምዶት ‹ምናለ በልተው እንኳን ቢሠሩ› እያለነው፡፡›› የዐጸደ ሕጻናት አማርኛ ማስተማሪያ ይመስል ‹‹ጋን በጠጠር ይደገፋል›› የሚለውን አባባል ለማሳየት ጠላ የሞላ ጋን ማሳየት ያስፈልጋል? ግድቡ አሳዘነኝ፡፡ ‹እብድ የያዘው መልክ አይበረክትም› ማለት ይኼ ነው፡፡ 
 
ልጅቱ የሐር ነዶ የመሰለ ፀጉር ነው ነበራት አሉ፡፡ አልፈለገችውም፡፡ ፀጉር ቤት ገባችና ‹‹ቁረጭኝ›› አለቻት ፀጉር ሠሪዋን፡፡ ከከፈለቻት እርሷ ምን ተዳይዋ ልትመደምዳት ተነሣች፡፡ እዚያ ፀጉር ቤት ልትሠራ ገብታ የነበረች እናት ብትመክራትም ወጣቷ እምቢ አለች፡፡ ሴትዮዋም ‹‹ ይህን የመሰለ ፀጉር ማን እንዲህ ባለ ጭንቅላት ላይ ብቀል ብሎታል› አለች አሉ፡፡  
ሲሆን ‹በባሕል ትክክል ለመሆን› በዚህ ከፊሉ ሕዝብ በሚጾምበት ጊዜ የጥብስ ማስታወቂያ ባይኖር ጥሩ ነበር( የግድ መጠበስ ካለበት ወይም ጥብሱ በስፖንሰር የመጣ ካልሆነ)፡፡ ደግሞስ ከመቼ ወዲህ ነው ለገንቦ ጠላ የሚጋደሉ ጠጪዎች ሀገራዊ ለውጥ አምጥተው የሚያውቁት? ‹ዶሮ ብታልም ጥሬዋን› ሆኖ ካልሆነ በቀር፡፡ የሦስት ብር ሎተሪ ለማስቆረጥ በገንቦ ጠላ መጣላት አመልን በቴሌቭዥን መግለጥ ካልሆነ ምን ሊሆን ነው፡፡
 
ወይ ግድቡን ‹የሕዳሴ ግድብ› ብለን መጥራታችንን እናቁም፤ ወይ ማስታወቂያዎቻችን ግድቡን የሚመጥኑ ይሁኑ፡፡ ያን የመሰለ ታላቅ ሐሳብና የትውልድ ሥራ በገንቦ ጠላ፣ በብረት ምጣድ ጥብስ፣ በጉንጭ ሙሉ ዳቦ መቀለጃ አታድርጉት፡፡   


click here for pdf

የዚህች ሀገር ባለቤቶች ሁላችንም ካልሆንን በቀር በተናጠል ማንም ባለ ግዛት ሊሆን አይችልም፡፡ ሉሲ አማራ ትሁን ኦሮሞ፣ አፋር ትሁን ሶማሌ፣ ጉሙዝ ትሆን ትግሬ፣ ወላይታ ትሁን ጋሞ የሚያውቅ የለም፡፡ በአኩስምና አካባቢው በተገኙ የድንጋይ ላይ ጽሑፎች ነገሥታቱ የሚገዙትን ሀገር ሕዝቦች ስም ይዘረዝራሉ፡፡ እጅግ የሚገርመው ግን ዛሬ በኢትዮጵያ ፖለቲካና የግዛት ይገባኛል ጥያቄ የምንሻኮተው ብዙዎቹ ጎሳዎች/ነገዶች ስማችን የለም፡፡ ሁላችንም ለማለት በሚያስደፍር መልኩ ከተለያየ ቦታ መጥተን የሠፈርንበት ላይ ረግተን ነው ዛሬ የምንገኘው፡፡ የሕዝብ የሥፍራ ንቅናቄ የታሪኳ አንዱ መገለጫ በሆነቺው ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ ሌላውን ሀገርህ አይደለም፣ ክልልህ አይደለም፣ መሬትህ አይደለም እንደማለት ያለ ታሪካዊ ኃጢአት የለም፡፡ ትንሽ በታሪክ ወደኋላ ስንጓዝ ዛሬ ክልልና መንደር በመሠረትንበት ቦታ ሌሎች ሲኖሩበት እናገኛለን፡፡ አሁን የያዝነው ቦታ ከምእተ ዓመታት በፊት የሁላችንም አልነበረም፡፡ ሁሉም ሠፋሪ ነው፡፡ ነባር መሬቱ ብቻ ነው፡፡  
ኢትዮጵያ የምታዋጣን የሁላችን እንድትሆን አድርገን ከሠራናት ነው፡፡ እንደ አጥር ሠሪ እንስሳት(territorial animals)  ከዚህ በመለስ ማንም አይገባብኝም፡፡ እኔን ያልመሰለውን በዚህ አካባቢ ላየው አልፈልግም የሚለው ሂደት መጨረሻው መበጣጠስ ነው፡፡ የልዩነትን ያህል ተመሳሳይነት ሰፊ አይደለም፡፡ ተመሳሳይነት እጅግ ጠባብ ነው፡፡ አንድ ነኝ ብሎ በሚያስብ ‹ብሔርም ሆነ ብሔረሰብ› ውስጥ አያሌ ልዩነቶች አሉ፡፡ የጎሳ፣ የቤተሰብ፣ የአካባቢ፣ የእምነት፣ የፍላጎት፣ የርእዮተ ዓለም፣ የጾታ፣ የሀብት ደረጃ፣ የሥልጣን፣ ምኑ ቅጡ፡፡ ሁሉም ተመሳሳዩን ፍለጋ ከሄደ መጨረሻው ግለሰብ ነው፡፡ በሰውነት ክፍላችን እንኳን ተመሳሳያቸውን ከሚያገኙት ይልቅ የማያገኙት ይበልጣሉ፡፡ ሰው እንኳን በግለ ሰብእነት ሕልው የሆነው ልዩነትን በአንድ ኑባሬ ውስጥ በማስተናገድ ችሎታ ነው፡፡ አንድን አካባቢ ‹በተመሳሳይነት ሚዛን› አንድነቱን ጠብቆ ማቆየት አይቻልም፡፡ 

ያማ ቢሆን ኖሮ ሶማልያን የመሰለ ጠንካራና የማይናወጥ መንግሥት አይኖርም ነበር፡፡በእምነትና በቋንቋ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ይሄ ተመሳሳይነታቸው ግን አንድነታቸውን ሊጠብቅላቸው አልቻለም፡፡ ትኩረታቸው ‹ተመሳሳዩን ብቻ ፍለጋ› በሚለው ላይ ስለነበር ወደ ነገድ፣ ወደ ጎሳ፣ ወደ ጎጥ፣ ወደ ቤተሰብ እየወረዱ ነው በጦርነት ሲታመሱ የኖሩት፡፡ ለሶማልያ ችግር መፍትሔው ተመሳሳይን መፈለግ አይደለም ልዩነትን ለማስተናገድ መቻል ነው፡፡ ተመሳሳይነት ጠባብ ነውና፡፡ ጠባብነት ከሚመነጭባቸው ምንጮች አንዱም ‹ተመሳሳይን ብቻ ፍለጋ› ነው፡፡
የዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዛሬ በሚታወቅበት ቦታ ላይ ከተገደመ ከ700 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ በዚያ አካባቢ አያሌ መንግሥታትና ሕዝቦች ተፈራርቀዋል፡፡ ገዳሙ ግን መከራ ሲገጥመው እየቀዘቀዘ፣ መከራውን አሸንፎ ደግሞ እንደ ፍግ እሳት እንደገና እየጋመ ከእኛ ዘመን ደርሷል፡፡ ወደዚያ ገዳም የሚገቡ መነኮሳት ሰማያዊቷን ሀገር የሚናፍቁ፣ ጾምና ጸሎትን ገንዘባቸው ያደረጉ፣ የጻድቁን ቃል ኪዳን የሚጠብቁ ናቸው፡፡ የመነኩሴ ሀገር የለውም፡፡ መነኮሳት እንኳን ከእናትና አባታቸው በተወለዱበት ሀገር ቀርቶ ስማቸውና ታሪካቸው በማይታወቅበት ሀገርም ‹ሀገርህ የት ነው?› አይባሉም፡፡ 
ኢትዮጵያውያን መነኮሳት ግብጽ ውስጥ ኖረዋል፣ ሊባኖስ ውስጥ ኖረዋል፣ ሶርያ ውስጥ ኖረዋል፤ ግሪክ ውስጥ ኖረዋል፣ ሮም ውስጥ ኖረዋል፡፡ አርመን ውስጥ ኖረዋል፡፡ ‹ሙሳ አል ሐበሽ› ሶርያ ውስጥ የታወቀ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ ነው፡፡ የሶርያ ድርሳናት እንደሚነግሩን ሙሳ (ሙሴ) የዐፄ ገብረ መስቀል ልጅ ነው፡፡ ዛሬ ከኢትዮጵያ በላይ ሀገሩ ሶርያ ናት፡፡ በቅርብ ዓመታት የኢትዮጵያውያን መነኮሳት ገዳም በሊባኖስ ውስጥ በቁፋሮ ተገኝቷል፡፡ ቫቲካን ውስጥ የኢትዮጵያውያን መነኮሳት ማረፊያ ለታሪክ ቆሞ ይታያል፡፡ አርመን ውስጥ ኤቺሚዚን የአቡነ ኤዎስጣቴዎስ ገዳም ዛሬም አለ፡፡ 
እንዲያውም ዛሬ የዝቋላ መነኮሳት እንደገጠማቸው ያለ ‹ሀገርህ አይደለም› የሚል ሰውነት ያልገባው ፈተና ሲገጥማቸው ራሱ ፈጣሪ ነበር ይገሥጽላቸው የነበረው፡፡ በተአምረ ማርያም ላይ የተጻፈውና ኢየሩሳሌም በጦርነት ምክንያት በተዘጋች ጊዜ በ13ኛው መክዘ አካባቢ ወደ ኢየሩሳሌም የተጓዘው ኢትዮጵያዊ ታሪክ ለዚህ ማሳያ ሆኖ ይኖራል፡፡ ይህ በኢየሩሳሌም ተሳላሚዎች ሁሉ የታወቀውና ዛሬም ድረስ በጎልጎታ መግቢያ በር ላይ ምልክቱን ትቶ ያረፈው ታሪክ እንዲህ ነበር የተፈጸመው፡፡
ከዛሬ 700 ዓመታት በፊት አንድ ኢትዮጵያዊ ወደ ኢየሩሳሌም ይጓዛል፡፡ ከአፍሪካ ምድር የሄደ ብቸኛ ሰው ነበር፡፡ የትንሣኤ በዓል ሲከበር የትንሣኤውን መብራት ከመቃብሩ የሚያወጡት ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ ያን ጊዜ ግን ብቻውን ስለነበር ማንም ከቁም ነገር አልቆጠረውም፡፡ እንዲያውም  በመልኩ ምክንያት ተንቆ ‹ያለ ሀገርህ ለምን መጣህ፣ ውጣ› ተባለ፡፡ እርሱም ወጥቶ መግቢያው በር ላይ ሲያለቅስ በላዩ ላይ የብርሃን ዓምድ ተተክሎ ታየ፡፡ ተሳላሚው ሁሉ እምነቱንና ታላቅነቱን አደነቀ፡፡ ብርሃኑ የወረደበት ቦታም ተሰንጥቆ እስከ ዛሬ ድረስ ይታያል፡፡ ወደ ጎልጎታ የሚገባም ሁሉ ይሳለመዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን መነኮሳት በሌሎች ሀገሮች ሄደው በኪደተ እግራቸው የባረኩት ሁሉ ሀገራቸው ሆኖ መኖራቸው ብቻ አይደለም የሚገርመው፡፡ ከመላው ዓለም የመጡ መነኮሳትም በዚህች ሀገር ውስጥ ‹ከየት መጣችሁ? የማንስ ወገን ናችሁ?›› ተብለው ሳይጠየቁ እንደ ሀገሬው ዜጋ ኖረዋል፡፡ አባ መጣዕ(ሊባኖስ)፣ ተሰዓቱ ቅዱሳን፣ አርባ ሐራ፣ አምስቱ የመንዝ ቅዱሳን፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ እጨጌ ዕንባቆም፣ ማኅበረ ጻድቃን፣ እነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያ መጥተው ኖሩ፡፡ እዚህችም ሀገር ዐረፉ፡፡ ገዳማቸው ገዳማችን፣ ታሪካቸው ታሪካችን ሆነ፡፡ 
ዛሬ ያ ሁሉ ተረስቶ ነው የዝቋላ ገዳም መነኮሳት ዝቋላ ‹ሀገራችሁ አይደለም›› የተባሉት፡፡ ለመሆኑ እነዚህ ሰዎች ኢትዮጵያውያን አይደሉምን? እዚህ ቦታኮ ከ700 ዓመታት በላይ ኖረዋል፡፡ እዚህ አካባቢ ከ700 ዓመታት በፊት የነበሩ ዜጎች አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሲመጡ ‹ኦቦ› ብለው ተቀበሏቸው እንጂ ‹ሀገርዎ አይደለም ይውጡ› አላሏቸውም፡፡ ዛሬ በሥልጣን ላይ ካሉትና ገዳሙን በኢሬቻ መተካት ከሚፈልጉት ሰዎች ይልቅ ያኔ የነበሩት ሰዎች ልበ ሰፊዎች፣ አስተዋዮች፣ የሰውነት ክብር የገባቸው፣ የሀገርን ትርጉም የተረዱ፣ ከዘር ይልቅ ለሰውነት ታላቅ ቦታ የሚሰጡ፣ ሰውን በምግባሩ እንጂ በቋንቋውና በቀለሙ፣ በዘሩና በአጥንቱ የማይለኩ ነበሩ፡፡ 
የአንድ ክልል የቱሪዝም ቢሮ አንድን ገዳም ነጥቆ በገዳሙ ሥርዓት የማይፈቀድ ሌላ እምነትን ለመተካት ማነው ሥልጣን የሰጠው? በዚያ ገዳም ክልል ውስጥ ሊከበሩ የሚገባቸው ሃይማኖታዊ በዓላትንስ በምን ቀኖናዊ ሥልጣኑ ነው የሚወስነው? ለምንስ ነው እነዚህን መነኮሳት እየጠራ የሚያስፈራራው? ይኼ ገዳምኮ ዘመናትን ሁሉ ተሻግሮ እዚህ እንዲደርስ ያደረገው በእምነቱ ጽኑ የሆነው የአካባቢው የኦሮሞ ተወላጅ ነው፡፡ ሕዝቡ እዚያ ገዳም ለጸሎት የተጉ መነኮሳት እንደሚገኙ፣ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የቃል ኪዳን ቦታ እንደሆነ የሚያምን ነው፡፡ በየዓመቱ በጥቅምትና በመጋቢት 5 ወደ ቦታው በመሄድ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዓል ከሚያከብረው ሕዝብ አብዛኛው የአካባቢው የኦሮሞ ተወላጅ ነው፡፡ ታድያ እነዚህ አካላት ይህንን አስተሳሰብ ከየት አመጡት? 
ይኼ ተልዕኮ ሃይማኖታዊ ተልዕኮ አይደለም፡፡ የጠብ ጫሪነት ተልዕኮ ነው፡፡ በሰላም የኖረውን ሕዝብ የማበጣበጥ ተልዕኮ ነው፡፡ መጋቢት 5 ቀን በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዓል ‹ኢሬቻን በጠበሉ ቦታ እናከብራለን፣ ሐውልት እናቆማለን› ብሎ በሕዝብ መገናኛ ማወጅ ጠብ ያለሽ በዳቦ እንደማለት ነው፡፡ ማንኛውም ሰው ያጸድቀኛል ብሎ ያሰበው እምነት ሊከተል ይችላል፡፡ ሁለት እምነቶች ግን በአንድ ቤተ መቅደስ ሊመለኩ አይችሉም፡፡ ሁሉም የየራሱን ነው መከተል ያለበት፡፡ ‹ከባልሽ ባሌ ይበልጣልና አልጋሽን ልቀቂለት› የሚለው ብሂል ግን ዛሬ የሚያዋጣ አይመስልም፡፡ የሃያ አንደኛው መክዘ ኢትዮጵያንም በጤና አውሎ አያሳድራትም፡፡ በዝቋላ ገዳም ላይ የተጀመረው ርስትን የመንጠቅ ሥራም በዝቋላ የሚያበቃ አይሆንም፡፡ ‹መንግሥታዊ ሃይማኖት የለም› ከተባለ መንግሥታዊ መዋቅሮች አንድን እምነት ደግፈው ሌላውን እምነት ለመጫን እንዴት ቻሉ? 
ስለዚህም
1.      ቅዱስ ፓትርያርኩ ሁኔታውን በተመለከተ ለሚመለከታቸው ድብዳቤ  መጻፋቸው የሚገባ ቢሆንም ቅዱስ ሲኖዶስ ግን ይህንን ነገር በዕንቁላሉ ለመቅጨት መወሰንና መሥራት ያለበት ጊዜ ዛሬ ነው፡፡ መነኮሳቱና ሀገረ ስብከቱ የጻፏቸው ደብዳቤዎች በገዳሙ ስለደረሰው መከራ ብዙ የሚናገሩት ነገር አለ፡፡ በስብሰባዎች የደረሰባቸው ጫና፣ በየጊዜውም የሚደርስባቸውን እንግልት ገልጠውታል፡፡ ሲኖዶሱ ገዳማትን ከመጠበቅ የሚቀድም ሌላ ኃላፊነት የለውም፡፡  
2.     ምእመናንም ገዳሙን በንቃት መከታተልና በተለይም በመጋቢት 5 ቀን በክብረ በዓሉ በመገኘትና በዓሉን በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት በማክበር ለቅዱሱ ሥፍራ ያለንን ፍቅር፣ ለመነኮሳቱ ያለንን የዓላማ አንድነት፣ ሁላችንንንም ለሚያቅፈው ኢትዮጵያዊነት ያለንንም ክቡር ሥፍራ ማሳየት አለብን

3.     መንግሥትም በጥባጭ ካለ ጥሩ ለመጠጣት አይቻልምና በሚዲያ የተሳተው በሚዲያ፣ በአሠራር የተበላሸውም በአሠራር እንዲታረም ማድረግ ይገባዋል፡፡ 
                  

ለሁለት ተከታታይ ጊዜ የተካሄደው የዓመቱ በጎ ሰው ሽልማት የ2007 የምርጫ ሂደት የካቲት 12 ቀን 2007 ዓም በካፒታል ሆቴል በተዘጋጀ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ተጀመረ፡፡  
ጋዜጠኞች፣ የቀድሞ ተሸላሚዎችና እጩዎች፣ ታዋቂ ሰዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በተከናወነው የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ስለ በጎ ሰው ሽልማት ያለፉት ዓመታት ክንዋኔዎችና ያመጣቸውን በጎ ተጽዕኖዎችን በተመለከተ ገለጻ ተደርጓል፡፡ የሽልማት ኮሚቴው አካላት እንደገለጡት 2007 ዓም የሽልማት ሂደት ካለፉት ዓመታት በተለየ በ10 ዘርፎች የሚከናወን ሲሆን ሂደቱ ተጠናቅቆ ሽልማቱ የሚሰጠው በነሐሴ ወር መጨረሻ ላይ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከጥቆማው በኋላ የእጩዎችን ዝርዝር መግለጫ የማዘጋጀት ሥራ የሚሠራ ሲሆን፣ በመቀጠልም በየሞያው ዕውቀትና ብስለት ባላቸው ሰዎች በተቋቋ ቡድኖች የመጀመሪያ አላፊዎች የመረጣ ሥራ ይከናወናል፡፡ በመቀጠልም ማጣሪያውን ላለፉት የሕይወት ታሪክ ዝግጅት ሥራ ይከናወናል፤ በማስከተልም ቦርዱ የመጨረሻዎቹ ተሸላሚዎች ላይ ውሳኔ ይሰጣል፡፡
ለጠቋሚዎች የተሻለ ዕድል ለመፍጠር የኢሜይል፣ የስልክ፣ የፖስታና የገጸ ድር የመጠቆሚያ መንገዶች የተዘጋጁ ሲሆን፣ የበጎ ሰው ገጸ ድር እዚያው በእዚያው(አውቶማቲክ) የሆነ የእጩ መጠቆሚያ ቅጽ ዝርዝር መረጃዎችን ይዟል፡፡
ለሀገራቸውና ለወገናቸው የሠሩ፣ አኩሪ ገደል የፈጸሙ፣ ለትውልዱ አርአያ የሚሆኑና የሀገራቸውን ክብር ከፍ ያደረጉ ዜጎችን በመጠቆም ሕዝቡ እንዲሳተፍ፤ ጋዜጠኞችና በማኅበራዊ ሚዲያ የላቀ ተሳትፎ ያላችሁ ዜጎች መረጃውን በማዳረስ፣ የኢንተርኔት አገልግሎት ለማያገኙም አትሞ በመስጠት ሁሉም እንዲተባበር ቦርዱ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

 

የዕጩ መጠቆሚያ ዘርፎች
1.      ሰላም፡- በዚህ ዘርፍ ለሀገራዊ ሰላም፣ ለሕዝቦች መግባባት፣ ለግጭቶች መፈታት፣ ማኅበረሰቡ ላቅ ያለ ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲያገኝ በማድረግ የሠሩ ይሸለማሉ
2.     ሳይንስ፡ በሕክምና፣ በቴክኖሎጂ፣በፊዚክስ፣ በኬሚስሪ፣ በምሕንድስና፣ በአርክቴክቸር፣ ወዘተ የሠሩ ይሸለማሉ
3.   ኪነ ጥበብ በልዩ ልዩ የኪነ ጥበብ ዘርፎች በአዲስ መንገድ፣ በልዩ አቀራረብ፣ የሥነ ጽሑፍን ደረጃ ከፍ ያደረጉ፣ በማኅረሰቡ ዘንድ በጎ ተጽዕኖ የሚያሳድር ሥራ የሠሩ፣ ለኪነ ጥበባችን ዕድገት የተጉ ዜጎች ይሸለማሉ
ሀ. ፊልም
ለ. ሙዚቃ
ሐ. ሥነ ጽሑፍ
መ. ቴአትር
ሠ. ሥዕልና ቅርጻ ቅርጽ
4.     የበጎ አድራጎት ሥራዎች፡- በርዳታና ሰብአዊ አገልግሎት የሠሩ ይሸለማሉ
5.     ግብርና ንግድና የሥራ ፈጠራ፡- በንግድ(ቢዝነስ)፣ በግብርና እና ለሕዝብ የሚጠቅሙ ሥራዎች በመፍጠር፣ አዳዲስ የሥራ ሐሳቦችን በማመንጨት የሠሩ ይሸለማሉ
6.     ስፖርት፡- በስፖርቱ መስክ አርአያነት ያለውና በጎ ተጽዕኖ የሚያመጣ ሥራ የሠሩ ይሸለማሉ
7.     መንግሥታዊ የሥራ ኃላፊነትን መወጣት፡- በተመደቡበት መንግሥታዊ የኃላፊነት ዘርፍ አርአያ የሚሆን ለውጥ ያመጡና ተገቢውን ሕዝባዊ አገልግሎት የሰጡ
8.     ማኅበራዊ ጥናት፡በማኅበራዊ ጥናት መስክ ተሠማርተው የኅብረተሰቡን ማኅበራዊ ችግሮች የሚፈቱና አዳዲስ ግንዛቤ የሚያመጡ፣ ዕውቀት የሚጨምሩ ላቅ ያሉ ሥራዎችን የሠሩ ይሸለማሉ
9.     ሚዲያና ጋዜጠኝነት፡በሚዲያና በጋዜጠኝነት መስክ ለውጥ አምጭና በጎ ተጽዕኖ አሳዳሪ ሥራ የሠሩ ይሸለማሉ
10.   ቅርስና ባሕል፡-ቅርስና ባሕልን በመጠበቅ፣ በማስተዋወቅ፣ በመሰነድና ዓለም ዐቀፍ ዕውቅና እንዲያገኝ በመሥራት ለውጥ ያመጡ ይሸለማሉ፡፡


የመጠቆሚያ መመዘኛዎች
1.      የሚጠቆመው እጩ በሕይወት ያለ ኢትዮጵያዊ ሰው ወይም ተቋም መሆን አለበት
2.     የምንጠቁማቸው ኢትዮጵያውያን በጎ ለውጥ አምጭ የሆነ ሥራ የሠሩ መሆን አለባቸው፣
3.     የዜጎችን ሕይወት በማሻሻልና ሀገርን በማሳደግ ሊጠቀስ የሚችል ነገር ያከናወኑ መሆን አለባቸው፣
4.     አንድ ሰው በተለምዶ ሊሠራው ከሚገባው ወይም ከሚችለው ሥራ ላቅ ያለ ሰብእና የሚታይበት ተግባር የፈጸሙ መሆን አለባቸው፤
5.     በአሠራር፣ በአስተዳደር፣ በጥናትና ምርምር፣ በኪነ ጥበብና በማኅበራዊ አገልግሎት አዲስ መንገድ ያመላከቱ፣ አዲስ አሠራር የዘረጉ መሆን አለባቸው፣
6.     የሀገርና የሕዝብን ችግር የፈታ ተግባር የከወኑ መሆን አለባቸው
7.     በተሠማሩበት መስክ መሥዋዕትነት ጠያቂ ግዳጅን የተወጡ፣ ራሳቸውን ለሀገርና ለወገን የሰጡ መሆን አለባቸው
8.     ይሁነኝ ብለው የሀገርንና የወገንን ስም የሚያስጠራ፣ ታሪካችንን፣ ባሕላችንን፣ ቅርሳችንን አጉልቶ የሚያወጣ የዜጋ ሥራ የሠሩ መሆን አለባቸው
9.     የማኅበረሰቡን ሞራላዊና ሥነ ምግባራዊ እሴቶችን ለሌሎች መጥፎ ምሳሌ በሚሆን መንገድ ያልጣሱና  ለትውልዱ አርአያ ሊሆኑ የሚችሉ መሆን አለባቸው
10.   በተቻለ መጠን ከዚህ በፊት ሥራቸው ሊነገር፣ ሊዘከርና ሊታወቅ ያልቻለ
11.      ለሀገሪቱ ዕድገትና ሥልጣኔ ለውጥ አምጭ አስተዋጽዖ ያደረጉ
12.    ለሌሎች አርአያ የሚሆኑ ብቁ አመራሮችን የሰጡ፣ በአመራሮቻቸውም አካባቢያቸውን፣ ድርጅታቸውንና መሥሪያ ቤታቸውን የለወጡ፣
13.    አዲስ፣ የራሱ ወጥነት ያለውና ያልተደፈረ የሚመስለውን ሥራ ያከናወኑ፣
14.   የሀገሪቱን ክብርና ደረጃ ያስጠበቁ፣ የሀገሪቱንም መብት ያስከበሩ፣
15.    ሀገራቸውን በዓለም አደባባይ በበጎ ያስጠሩ፣ ስሟን ከፍ ያደረጉ
የመጠቆሚያ አድራሻዎች
              ስልክ፡- 0941615252
              ኢሜይል፡- [email protected]
              ገጸ ድር     www.begosew.com
             ፖስታ፡- 150035  
የመጠቆሚያው ጊዜ
ከየካቲት 13 እስከ መጋቢት 12 ቀን፣ 2007 ዓም ድረስ
 ዕጩዎችን በሚጠቁሙበት ጊዜ
1.      የተጠቋሚዎችን ሙሉ ስም ይጻፉ
2.     የሚገኙበትን ልዩ ቦታ ይግለጡ
3.     የሠሩትን ሥራ በአጭሩ ይግለጡ
4.     ስለ ተጠቋሚው ተጨማሪ መረጃ ሊገኝ የሚችልበትን ምንጭ ይጠቁሙ
5.     ከተቻለ የስልክና የኢሜይል አድራሻቸውን ይግለጡ
6.     የራስዎንም አድራሻ ይግለጡ(ተጨማሪ መረጃ ለመጠየቅ)
7.     ስለሚጠቁሙት ዕጩ ተጨማሪ መረጃ ሊሰጡን ከቻሉ በኢሜይል ወይም በገጸ ድራችን ያያይዙልን

ከቀናት በፊት ሬዲዮ ማዳመጥ እስኪሰለቸን ድረስ ሁሉም ጣቢያዎችና ፕሮግራሞች ስለ ‹ቫላንታይን ደይ› ነበር የሚወተውቱን፡፡ ልክ ፍቅር በዚህች ሀገር እንዳልተወለደ፣ ድኾ እንዳላደገ፣ ለወግ ለመዓርግ ደርሶ ጎጆ እንዳልቀለሰ ይመስል ነበር፡፡ ቀይ ልብስ ያልለበሰ፣ አበባ ያልያዘ፣ በምሽት በሚደረጉት ጭፈራዎች ያልተገኘ፣ ማታም ጥንድ ሆኖ አልጋ ያልያዘ ሰው ሁሉ ፍቅርን እንደማያውቅ ተደርጎ ነበር የሚተረክልን፡፡
ዝንጀሮ ጠባቂ ላያድር ያመሻል፣
አፌ ፈራሽ እንጂ ልቤስ ከጅሎሻል፤
ዝንጀሮ ጠባቂ ላያድር ካመሸ
ከፈራህኝማ ነገር ተበላሽ፡፡
                      ተብሎ ያልተገጠመ፤
አቡኪ ወእምኪ ኢይፈቅዱ እንግዳ
ሰዐምኒ ንሑር በሳንቃው ቀዳዳ፤ 

ያልተባለ ይመስል ነበር በዚህች ሀገር፡፡ ‹ፍቅር እዚህ ቦታ ፈገግ ብሎ ነበር› አለ ኤፍሬም ሥዩም፡፡ መቼም ፈገግ ካለባቸው አጋጣሚዎች መካከል አንዱ በቀደም ጋዜጠኞቻችን ‹ፍቅር የመጣውኮ ከውጭ ሀገር ነው› ሊሉን ሲደርሱ ሰምቶ መሆን አለበት፡፡

ምዕራባውያን በአንድ ነገር ጎበዞች ናቸው፡፡ ባሕላቸውን ወደ ሸቀጥነት መቀየርና የገበያ ማሟሟቂያ ማድረግ ይችሉበታል፡፡ የካፒታሊስት ሥርዓት አንዱ መገለጫውም ሁሉን ነገር ሸቀጥ ማድረግ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ለእነርሱ ሃይማኖት እንኳን ቢሆን ሲታመንበት ሳይሆን ሸቀጥ ሆኖ ሲሸጥ ነው የሚያዋጣው፡፡ ‹የቫላንታይን ደይ›ን በዓል ከፍቅረኞች በላይ ባለ ሆቴሎችና ባለ ጭፈራ ቤቶች፣ አበባ ሻጮችና የስጦታ ካርድ አምራችና አከፋፋዮች፣ ቸኮሌትና ወይን አምራቾች ይፈልጉታል፡፡ እነርሱ ፍቅርን በእሴትነቱ ሳይሆን በሸቀጥነቱ ነው የሚፈልጉት፡፡ የሚሞቱለት፣ የሚሠዉለት ዓይነት ፍቅር ሳይሆን የሚያተርፉበት ዓይነት ፍቅር፡፡ እንዲያውም አንዳንድ የሚዲያ ባለቤቶች ስለ ቫለንታይን ሂስ ለማቅረብ የሚነሡ የፕሮግራም አዘጋጆችን ‹‹ስፖንሰሮቻችን ይቀየማሉ› በሚል ሲከላከሉ እንደነበር ውስጥ ዐዋቂዎች ይናገራሉ፡፡
ፍቅር እንደ ሸቀጥ ስለታየ ‹ቀይ ልብስ ለብሳችሁ ከመጣችሁ የክብር ሥፍራ አለን፣ ጥንድ ሆናችሁ ከመጣችሁ ቅናሽ እናደርጋለን፣ እኛጋ ጥንድ ሆናችሁ አልጋ ከያዛችሁ ግብዣ ላይ ዋጋ እንቀንሳለን› የሚሉ ዓይነት ማስታወቂያዎች ነበሩ አየሩን የሞሉት፡፡
ኢትዮጵያውያን ከውጭ መልካም ሐሳብ የያዙ በዓሎችን ሲያመጡ ሐሳቡን እንጂ ሙሉ ቅርጽና ይዘቱን አያመጡትም፡፡ ገና ኢትዮጵያዊ መልክ ነው ያለው፤ ግን ዓለም ዐቀፋዊ በዓል ነው፡፡ የጥምቀት በዓል በሌሎችም ክርስቲያን ሕዝቦች ዘንድ አለ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ኢትዮጵያዊ ቁመና፣ መልክና ባሕል አለው፡፡ የደብረ ታቦር በዓል በሌላውም ዓለም ይከበራል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ቡሄ ሆኗል፡፡
ይህ መሆኑ በሦስት ነገር ሲጠቅመን ኖሯል፡፡ በአንድ በኩል የራሳችን መገለጫ፣ የማንነታችን ማነጫና መግለጫ ሆኖ እንዲኖር አድርጎታል፡፡ ለዚህ ነውኮ መስቀልን አዲስ አበባ፣ ገናን ላሊበላ፣ ጥምቀትን ጎንደር ላይ ለማየት የአገር ፈረንጅ የሚጎርፈው፡፡ እዚያ የሚሄደው ኢትዮጵያዊውን መልክ ለማየት እንጂ ጌታ መወለዱን፣ መጠመቁንና መስቀሉ ከተቀበረበት መገኘቱን እንደ አዲስ ለመማር አይደለም፡፡ ይህን ሐሳብ ወደ ሕልው ባሕል የቀየርንበትንና ያንንም የጠበቅንበትን መንገድ ለማየት እንጂ፡፡ አንድን ሐሳብ የሕዝብ ባሕል ማድረግ በሰው ልጅ ጉዞ ውስጥ ወሳኙና እጅግ አስፈላጊው የሰብእና ክፍል ነው፡፡ 
በሌላ በኩል ደግሞ ከኢትዮጵያዊ ማንነት ጋር የተዋሐደ በመሆኑ ገጠር ከከተማ፣ ሰሜን ከደቡብ ሳያነቅፈው ተጣጥሞ እንዲሄድ አድርጎታል፡፡ ከደኻ እስከ ሀብታም፣ ከማይም እስከ ምሁር፣ ከደቂቅ እስከ ሊቅ እንደ ዐቅሙ ያከብረዋል፡፡ ሦስተኛው ደግሞ በዓሉ ቤተኛ መሆኑ ነው፡፡ ቤተኛ በዓል ማለት ቤተሰብን የሚመለከት፣ ሁሉም የሚሳተፍበት፣ የሀገር ቤቱን ሰው ተሳትፎ የሚጠይቅ ማለት ነው፡፡ ለገና ዳቦ የሚሆነውን እህል፣ በግና ዶሮውን ገበሬ ያመጣል፤ ነጋዴ ለበዓሉ የሚያስፈልገውን ነገር ያከፋፍላል፡፡ የሴቶች ሞያ በጠላው በዶሮው፣ የወንዶቹ ሞያ በእርዱ በሥጋው ይታያል፡፡ እንኳን አደረሰህ የሚለው ዘመድ አዝማድ መልእክቱን ይልካል፡፡ ከጉልት ገበያ እስከ ‹ሱፐር ማርኬት› አገሩ ሸብ ረብ ይላል፡፡ በዓል መሆኑን አካባቢውም ይናገራል፡፡ ልጅ ዐዋቂው፣ ያገባው ያላገባው፣ ነባሩና አዲስ መሽራው፣ መናኙና ከተሜው፣ ሁሉም ይሳተፋል፡፡ ለዚህ ነው እነዚህ ሀገርኛ በዓላት የመከራ ዘመናትን ሁሉ አልፈው በየጊዜው እየበለጸጉ እዚህ ዘመን የደረሱት፡፡ 
 
እንደ እውነቱ ከሆነ የ‹ቫለንታይን ደይ› ኢትዮጵያኛ ሆኖ ቢሆን ኖሮ በየካቲት አበባዉ ሁሉ ረግፎ ባለቀበት በየካቲት  ወር አልነበረም መከበር የነበረበት፡፡ በጥቅምት እንጂ፡፡ አበባ መስጠት ያለባችሁ የግድ ገዝታችሁ ነው ካልተባልን በቀር፡፡ አገሩ በሙሉ በአበባ የሚያሸበርቅበትን የጥቅምትን ወር አሳልፎ የአበባን በዓል በመከር ጊዜ ማክበር ምን ያህል በዓሉ ኢትዮጵያዊነት እንደሚጎድለውና ተገንጥሎ ብቻውን እንደቆመ የሚሳየን ነው፡፡     
 
ምንም እንኳን ቀይ ሽብር፣ ቀዩ ጦር፣ የቀይ ኮከብ ጥሪ፣ የሚሉ መጥፎ የቀይ ቀለም ትዝታዎች ቢኖሩብንም ያ ሁሉ ቀይ ወይን፣ ቀይ ምንጣፍ፣ ቀይ መብራት፣ ቀይ አበባ፣ ለጦርነት፣ ለሽብርና ለጠብ አይደለም፤ ለፍቅር ነውና ኩነቱን ሳይሆን ምክንያተ ክዋኔውን ተመልክተን ስለ ፍቅር አምላክ ስንል ይሁን ብለን እዚህ ላይ እንለፈው፡፡
 
ግን እስኪ ልክ እንደ ቫላንታይኑ ሁሉ ለራሳችንም ጉዳይ ትኩረት እንስጥ፡፡ አሁን ነገ የካቲት 12 ቀን ለዚህች ሀገር ሕይወታቸውን የገበሩ፣ በፋሽስቶች የተጨፈጨፉ፤ ዛሬ እኛ ዘና ብልን በቀይ ወይንና በቀይ ምንጣፍ የ‹ቫላንታይን ቀንን› እንድናከብር ያደረጉ ሰማዕታት በዓል  ይከበራል፡፡ ከቫለንታይን ይልቅ የካቲት 12 የራሳችን ጉዳይ ነው፡፡ ለዛሬ ማንነታችን ወሳኝ ምዕራፍ ነው፡፡ እንዲህ በነጻነት ቀና ብለን እንድንሄድ ዋጋ ከከፈሉ ሰዎች መካከል ናቸው የየካቲት 12 ሰማዕታት፡፡ ይኼው ዛሬ ዋዜማው ነው፡፡ ማንም ግን ስለ ነገው በዓል እየተናገረ አይደለም፡፡ ነገም ከአንዲት ዜና በቀር ማን ስለ ጉዳዩ ጣል እንደማያደርግ እገምታለሁ፡፡  
 
የትናንት ታሪኩን በሚገባ የማያውቅ፣ የማይተነትንና የማይገነዘብ የትናንቱን ስሕተቱን በከፋ መንገድ ለመድገም የተረገመ ነው፡፡ ከትናንት የተሻለ ለመሥራት በትናንቱ መሠረትም ላይ ለመገንባት ትውልድ የተሠራበትን የታሪክ ጡብ ማወቅ አለበት፡፡ በርግጥ እንደ ቫለንታይን ቀን በስፖንሰር አያንበሸብሽም፣ በርግጥም ቀይ ወይንና ቀይ ምንጣፍ የለውም፡፡ አበባ ለመሸጥና ጭፈራ ለመጨፈር አይመችም፡፡ ግን ከቫለንታይን ቀን ይልቅ የካቲት 12 ቀን እኛነታችን ነው፡፡ መነሻ የሌለው መንገድ፣ መንገድ የሌለውም መድረሻ የለም፡፡ ለመንገዱ ዋጋ ነሥቶ፣ ለመድረሻው ተስፋ ማድረግን የመሰለ ዕብደትም የለም፡፡ ለመንገድ ሠሪው ዋጋ ነሥቶ በመንገዱ ላይ ለሚሄደው መኪና ምስጋና ማዥጎድጎድን የመሰለ ክፉ ዐመል የለም፡፡ በትናንቱ ላይ ለመግባባት አለመቻላችን ነው በዛሬውም ላይ ሊያግባባን ያልቻለው፡፡ 
 
እናም እናንት ‹ሚዲያዎች›፣ እናንት በዓለ ሚዲያዎች
የኢትዮጵያ ነን ካላችሁ
እስኪ እንያችሁ
ኢትዮጵያዊ ለሆኑ በዓሎችና ጉዳዮች እንደ ቫለንታይን ቀን ሁሉ አገሩን በሚዲያ ስታውዱት፣ እንደ ቅዱስ ቫለንታይን ሁሉ ስለ የካቲት 12 ሰማዕታት፣ ስለ አድዋ ጀግኖች፣ ስለ ማይጨው ዘማቾች ስትተርኩ እንስማችሁ፡፡ 
 
የኢትዮጵያ ነን ካላችሁ
የኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ፣ ባሕሎች ላይ፣ ታሪኮች ላይ፣ በዓሎች ላይ፣ ጀግኖች ላይ፣ ቦታዎች ላይ አጥንታችሁ፣ አንብባችሁ፣  ስታቀርቡ እስኪ እንያችሁ፡፡
ርግጥ ነው ዊኪፒዲያ ላይ አይኖር ይሆናል፣ ኢንተርኔት ላይ በክሊክ አይገኝ ይሆናል፣ ጎልጉል ሲጎለጎል በቀላሉ አይመጣ ይሆናል፡፡ ግን የራሳችን ጉዳይ ነው፡፡ ‹ራሴን በራሴ ካላንቆለጳጰስኩት ማን ያንቆለጳጵስልኛል› ነውና እኛ ለእኛ እንሥራ፡፡ ሌሎችም ስለ ሠሩ ነው ዛሬ ስለ እነርሱ በቀላሉ የትም የምናገኘው፡፡ እኛም ብንሠራ የኛ ጉዳይ በቀላሉ እንዲደረስበት ማድረግ እንችላለን፡፡ 
 
የኢትዮጵያ ነን ካላችሁ
እስኪ እንያችሁ፤  

በአማርኛ ቋንቋ ዕድገትና ብልጸጋ ጎዳና ላይ ከሚገኙት ተግዳሮቶች አንዱ ተገቢ የሆነ፣ ሁሉም የሚቀበለው፣ በቀላሉ የሚገኝና ደረጃውን የጠበቀ የአማርኛ ሥርዓተ ጽሕፈት አለመኖር ነው፡፡ የአጻጻፍ መንገዶችን፣ መልክዐ ፊደልና ሥርዓተ ፊደልን፣ በቃላት አጻጻፍ የሆሄ መረጣን፣ የፊደል መጠንን፣ የስያሜ ቃላት አሰጣጥን፣ የትርጎማ መንገድን፣ ወዘተ የተመለከተ ሥርዓተ ጽሕፈት ያስፈልገናል፡፡ ለዛሬው ግን ብዙዎቻችን የምንስትበትንና የምንምታታበትን የሞክሼ ሆሄያት (ሀ፣ ሐ፣ ኀ፣ ኸ፤ ሠ፣ሰ፣ አ፣ ዐ፤ ጸ፣ ፀ) አጻጻፍን በተመለከተ ታዋቂው ሊቅ ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ(ነፍሳቸውን ይማርና) አዘጋጅተውት ሻማ ቡክስያሳተመውን ‹‹የአማርኛን ሞክሼ ሆሄያት  ጠንቅቆ ያለመጻፍ ችግርና መፍትሔ›› የሚለው መጽሐፍ ላስተዋውቃችሁ፡፡
መጽሐፏ የኪስ መጠን ብትሆንም እስከዛሬ በጉዳዩ ከተዘጋጁት የተሻለች፣ በአመክንዮ የቀረበችና በጥናት ላይ የተመሠረተች ናት፡፡ በተለይም ለደራስያን፣ ለቢሮ ጸሐፊዎች፣ ለፖለቲካ ሰዎች፣ ለጋዜጠኞች፣ ለማስታወቂያ ባለሞያዎች፣ ለአርታዕያን፣ ለፌስ ቡክ ደንበኞችና ለሌሎቻችንም በሞክሼ ቃላት ዙሪያ መመሪያ የምትሆን ናት፡፡ እባካችሁ ነገራችን ወጥ እንዲሆን በሊቁ መንገድ እንሥራ፡፡ ዋጋው 25 ብር ነው ገዝተን በጠረጴዛችን ላይ እናስቀምጥና እንመራባት፡፡
ከምር ሁላችንም ቤትና ቢሮ መጥፋት የሌለባት ናት፡፡

እስኪ ይኼንን በአንድ ትምህርት ቤት ለሦስተኛ ክፍል ተማሪ የቀረበ ፈተና ተመልከቱት፡፡ አሁን የሚወድቀው ማነው? ተማሪው ወይስ ራሱ ትምህርቱ? እስኪ የስሕተቱን ብዛት እዩት? ወይ በአፍ መፍቻ ቋንቋችን ተምረን ጽንሰ ሐሳቡን አልተረዳነው፣ ወይ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ተምረን ቋንቋውን በሚገባ አላወቅነው፤ ከሁለት ያጣን ሆንኮ፡፡ ለመሆኑ ፈተናው እንዲህ ከሆነ ትምህርቱማ ምን ሊሆን ነው? እንዲህ እያስተማርንና እየፈተንንስ ምን ዓይነት ትውልድ ይሆን የምናወጣው? ‹አለሽ መስሎሻል ተበልተሽ አልቀሻል› አለ ያገሬ ሰው፡፡

/ በርናንድ ብራድሊ አንደርሰን ልደቱ ቅድስት ካትሪን ደብር ጀማይካ ዉስጥ ነዉ፡፡ ወሩ መስከረም፣ ቀኑ 21 ዓመተ ምሕረቱ 1944 አቆጣጠሩ በአዉሮጳውያን፡፡ ቅድስት ካትሪን አጥቢያ ከእርሻዉ መካከል በር ያደገዉ፡፡ ዕድሜዉ ለትምህርት ሲደርስ ካሪቢያን ዉስጥ አንጋፋ ከሚባለዉና ከተከበረዉ ዎልማር የወንዶች ትምህርት ቤት ገባ፡፡ ወደ አሜሪካ ምድር የዘለቀው 1960ዎቹ ሲሆን በዋሽንግተን ዲሲ ዝነኛዉ ሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ በከፍተኛ ማዕረግ የመጀመሪያዉን የባችለር ዲግሪ አገኘ፡፡ ከክፍሉ ቀዳሚ ሆኖም ወደ ሕክምናዉ የትምህርት ዘርፍ ተሻገረ፡፡ ቀን ቀን ትምህርቱን እየተከታተለ፤  ሌሊቱን እየሠራና ራሱን እየረዳ ትምህርቱን ቀጠለ፡፡ 

.. 1970ዎቹ የመጀመሪያ ዓመታት ላይ በቀዶ ጥገና ሕክምና በከፍተኛ መዓርግ ተመረቀ፡፡ በትምህርትና በሥራ የበለጸገዉና ገና በለጋነቱ በትጋቱ የታወቀዉ፣ የቅርብ ጓደኞቹ በርኒ የሚሉት በርናንድ፤ የሕክምና ትምህርቱን ጨርሶ እንደተመረቀ ወደ ትዉልድ ሀገሩ ጃማይካ ተመልሶ በኪንግስተን የሕዝብ ሆስፒታል ማገልገል ጀመረ፡፡ ኪንግስተን የሕዝብ ሆስፒታል ነጻ ሕክምና የሚሰጥበት፣ ለተቸገሩና ዐቅም ለሌላቸዉ የሚለገስበት በመሆኑ ቀልቡን ገዛዉ፡፡ ወትሮም የሕክምና ሙያ ለአምሳያ ፍጡር የመድረስ መንፈስ አለዉና ከዶ/ በርናንድ አንደርሰን ዉስጣዊ ተፈጥሮና ተልዕኮ ጋር ገጠመ፡፡ / አንደርሰን ሕሙማንን ከማከም በላይ ተተኪ ወጣቶችን ማስተማርና ማዘጋጀትን እንደ ቃል ኪዳኑ ነበር የሚያየዉ፡፡
 እዚያም ጀማይካ ከሕክምናዉ ጎን ለጎን መምህር ሆኖ ብዙዎችን አሠልጥኗል፡፡ / በርናንድ የጃማይካ የሆስፒታል ተልዕኮዉን እንዳገባደደ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ ተመለሰ፡፡ ነገር ግን ሀብትና ዕድሉ ወዳላቸዉትርፍና ገንዘብ ወደሚጋበስባቸው ሆስፒታሎች ዓይኑን አላነሣም፡፡ እንዲያዉም የጤና ከለላና ሽፋን የሌላቸዉለመድረስ የሚችልበትን የቀድሞዉን ዲሲ ጄኔራል ሆስፒታል ነዉ የተቀላቀለዉ፡፡  ልዩ ተሰጥዖና ክህሎት ያለዉ / በርናንድ የሥራዉን ብቃትና የአመራር ችሎታዉን በዚያ ሆስፒታል ለማስመስከር ጊዜ አልወሰደበትም፡፡
 በዲሲ ጄኔራል ሆስፒታል በሊቀ መንበርነትና የቀዶ ጥገና ዳይሬክተር በመሆን ሆስፒታሉ በሀገሪቱዕዉቅና ያገኘ ሆስፒታል› ተብሎ እንዲጠቀስ ያደረገ ባለሙያ ነበር፡፡ ሲሠራ ውሎ ቢያድር ደከመኝ የማይል፣ሕሙማንን ማከም ተልዕኮዬ ነው› ብሎ የሚያምን ሰው ነበር፡፡ ዶ/ በርናንድ አንደርሰን መኖሪያዉን በመሠረተባት የአሜሪካ ርዕሰ መዲና ዲሲ፣ በሮድ አይላንድ መንገድ ላይ የግል የሕክምና ክሊኒክ መሥርቶ በመደበኛዉ ሥራዉ ላይ አከለበት፡፡ / በርናንድ ክሊኒኩን ሀብት በበዛበት መንደር ሳይሆን የችግረኞቹን ቀየ ፈልጎና ይሁነኝ ብሎ ነበር ያቋቋመዉ፡፡ የመክፈል ዐቅም የሌላቸዉ ሕሙማንን በዚያ ክሊኒኩ በራሱ ወጪ ሕክምና መስጠቱን ዛሬ ድረስ በምስጋና የሚያነሡት ብዙዎች ናቸዉ፡፡
/ር አንደርሰን ስሙ ሳይጠቀስ ለታይታም ሳይደርስ፣ ለተማረበት ትምህርት ቤት የአንድ መቶ ሺህ ዶላር ስጦታ የቸረ ለጋስ ሰው ነዉ፡፡ ይህ እንዲያውም ለአብነት ያህል ተነሣ እንጂ / አንደርሰን ‹ቀኝህ ሲሰጥ ግራህ አይመልከት› የሚለውን በተግባር ያሳየ፣  ልዩ ጸጋ የተጎናጸፈ ሰዉ ነበር፡፡ ዶክተር በርናንድ አንደርሰን ሕሙማንን መከባከብና ማከም፣ ችግራቸዉን ተቸግሮ፣ ቋንቋቸዉን ተናግሮ አምላክ የሰጠዉን ችሎታና በሰዉኛ የሚችለዉን ማድረግ የሕይወት ተልዕኮዉ ያደረገዉ ገና አንድ ፍሬ ወጣት እያለ ነዉ፡፡
አንድ ቀን ከሰዉ ዘር መፍለቂያዋ ከጥቁር ሕዝብ መኩሪያ ሀገር ኢትዮጵያ፤ እነ ማርክስ ጋርቬወደ ራሳችን እንመለስወዳሉባት ጥንታዊት ምድር ሄዶ የማገልገል ሕልም ነበረው፡፡ ያ ሕልሙና ራእዩ ይሳካ ዘንድ የኑሮ አጣማጁ ሲስተር እማዋይሽ ምክንያት ሆነችና ከምድረ አሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ለመጓዝ ሐሳብ ፀነሰ፡፡ 
ስለ ኢትዮጵያ ማንበብ፣ ስለ ኢትዮጵያ መመራመር ይወድ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ስም በተጠራበት ቦታ ሁሉ መገኘት አይሰለቸውም ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ይመሰጣል፡፡ ለሌሎች ወገኖቹ መንገርና ስለ ኢትዮጵያ እንዲያውቁ መጎትጎት ይወዳል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ማጥናት፣ ቤተ ክርስቲያን መሄድና ከአባቶች ጋር መወያያት ያስደስተው ነበር፡፡ የትዳር ጓደኛው ሲስተር እማዋይሽ ደግሞ ይኼ ደግ ሰው ኢትዮጵያ መጥቶ ይህንን የተከፈተ ልቡን ለሀገሯ ሰው ቢያስረክበው፣ ደግነቱን ቢያርከፈክፈው ትመኝ ነበር፡፤ መመኘትም ብቻ ሳይሆን ትጎተጉትም ነበር፡፡ 
‹‹ብዙ ጊዜ ሀገሬ ኢትዮጵያ ገብተን እንድንሠራ እነግረው ነበር፡፡ እርሱም በዚህ ላይ አስቦ እንደሚወስን ይገልጥልኛል፡፡ ከብዙ ጊዜ በኋላ አንድ  ማለዳ ‹ላንቺ አስደናቂ ዜና አለኝ› አለኝ፡፡ በጉጉት ጠበቅኩ፡፡ ‹ላንቺ ስል ወደ ኢትዮጵያ ልሄድ ወሰንኩ› አለኝ፡፡›› ትላለቺ ሲሰተር እማዋይሽ ያንን ቀን ስታስታውሰው፡፡
እርሱም አንድ አስቀደመና ታንዛኒያን፤ ኬኒያን ሄዶ ጎበኘ፡፡ አፍሪቃ የምትቃትትበትን፣  ጫንቃዋን የያዛት የትላንቱ የቅኝ ዛር እንዳልለቀቃት አይቶ አዘነ፡፡ አስከትሎም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣ የድህነቱና የችግሩን መክፋት ተመለከተ፡፡ ነገር ግን አዘነ እንጂ ሸሽቶ አልተመለሰም፡፡ ከአዉሮፕላኑ ሲወርድ አየሩን ሲምገዉልሙን አስታወሰዉ፡፡ የሕክምና ተቋማቱን ሲጎበኝ ሕሙማኑ ተኮልኩለዉ ቢመለከት ልቡ ተሰበረ፡፡ አዲስ አበባ ታላላቆቹ የግልና የመንግሥት የሕክምና ተቋማት ከእነርሱ ጋር እንዲሠራ ለመኑት፡፡ እርሱ ግን ወደ ገጠሩ መቅረብ ወደ ድኻው መጠጋት ይወድ ነበርና ከተሜዉን ጎብኝቶ ወደ ገጠሮቹ ሊመለከት አዘገመ፡፡ የሐኪም እጅ ማየት ቀርቶ መልኩና ገጹ የናፈቃቸዉ ወገኖች አጋጠሙት፡፡ በርካታ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጠዉ መጥተዉ ከየሆስፒታሉ ደጃፍ ተኮልኩለዉ አምላካቸዉን እየተማጠኑ፤ ከዕለታት አንድ ቀን የሐኪም እጅ እንዲነካቸዉ ሳምንታትን የሚጠብቁ ምስኪኖች ልቡን ነኩት፡፡ መንፈሱን ሳቡት፡፡ ጎንደርም በፍቅሯ ነደፈቺዉ፡፡ ቅርልኝ አለቺዉ፡፡ ዕድሜዉ ከግማሽ ምእተ ዓመት በላይ ለሆነዉ ለጎንደር ሆስፒታልና የሕክምና ኮሌጅ እጁን ሰጠ፡፡ / በርናንድ አንደርሰን የዋሽንግተን ዲሲዉን ስመ ጥር ሐኪም  የጎንደር እጆች አቀፉት፡፡ ፋታና ዕረፍት አላስፈለገውም፡፡ ወትሮም ዕረፍቱ፣ ቀድሞም ምቾቱ ለሕሙማን መድረስለተቸገረ ዋስ መሆን ነበረ፡፡ የቀናት ስምና ቁጥር ለዶ/ በርናንድ ዋጋ አልነበራቸዉም፡፡ ከአጸደ ሥጋ እስከተለየበት ጊዜ ድረስ ለእርሱ ቀናት ማለት የሥራና ሰዉን የማገልገያ ጊዜያት ናቸዉ፡፡ 
/ በርናንድ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የቀዶ ጥገና ትምህርት ክፍልን የተቀላቀለው በ1997 ዓም ነበር፡፡ / በርናንድ በኮሌጁና በሆስፒታሉ በነበረዉ ቆይታ የቅድመ እና ድኅረ ምረቃ ተማሪዎችን ከማስተማር ጎን ለጎን በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል ሕሙማንን በማከም ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድርጓል፡፡ በተለይም የቀዶ ጥገና ሕክምና ትምህርት ክፍል ሥርዓተ ትምህርት በየጊዜዉ እንዲሻሻል የነበረዉ የላቀ ሚና ምንጊዜም በትምህርት ክፍሉ አባላት ሊና የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ዶ/ በርናንድ ዕዉቅ ቀዶ ጥገና ሕክምና ባለሞያ እንደመሆኑ ያለዉን እጅግ ሰፊ ዕዉቀት፣ ክህሎትና ልምድ ለተማሪዎቹና ለሞያው ሰዎች በማካፈል በርካቶች በሞያዉ የተካኑ እንዲሆኑ ያለማሰለስ ሠርቷል፡፡ በተለይም የሆስፒታሉ የቀዶ ሕክምና ባለሞያዎች ብቻቸዉን ሊሠሯቸዉ የሚቸገሩ የጉበት ካንሰር፣ የጣፊያ ካንሰር፣ የልብና የደም ሥር፣  የመሳሰሉትን ቀዶ ጥገናዎች በማከናወን ሌሎቹ ልምድ እንዲቀስሙ ማድረጉ ለሞያዉ መጎልበት ከነበረዉ ከፍተኛ አስተዋጽ በተጨማሪ ሙማኑ ፈዉስ እንዲያገኙ ያደረገዉ ተኪ የለሽ ተግባር ከፈጣሪ የተላከ እስከመባል ያደረሰው ነበር፡፡
በበርናንድ ዘንድ ሥራ ሲያልቅ እንጂ ሰዓት ሲያልቅ ማቆም አይታሰብም፡፡ አንድ ቀን እንዲህ ሆነ፡፡ እርሱና ተማሪዎቹ ከጠዋት እስከ ማታ ቀዶ ጥገና ሲያደርጉ ዋሉ፡፡ ምሳ አልነበራቸውም፡፡ ልክ ፀሐይዋ ማቆልቆል ስትጀምር ጨረሱ፡፡ ጨርሰው ልብሳቸውን ሲያወልቁ ግን አንድ የገጠር ሰው አንኳኩ፡፡ ‹ወረፋ እየጠበቅኩ ነበር›› አሉ ረዳት ሐኪሙን፡፡ ‹‹አባቴ አሁንማ መሸ ነገ ይምጡ›› አላቸው፡፡ አማራጭ አልነበራቸውምና ከዘራቸውን አንሥተው ጉዞ ጀመሩ፡፡ በርናርድ ድምጽ ሰምቶ ወጣ፡፡ ረዳቱን ጠየቀው፡፡ ረዳቱም ያደረገውን ነገረው፡፡ በርናርድ አዘነ፡፡ ‹‹እንዲህ ነበር ያስተማርኩህ›› አለው ረዳቱን፡፡ ‹‹በል ቶሎ ተከትለህ ጥራቸው›› ሲል አዘዘ፡፡ ሰውየው ተጠሩና እንደገና ልብስ ተለብሶ ቀዶ ጥገናው ቀጠለ፡፡ ይኼ ረዳት ሐኪም ዛሬ ታዋቂ የቀዶ ጥገና ሐኪም ሆኖ እንዲህ አለ ‹‹ያንን ትምህርት ስላስተማረኝ ተመርቄ ሰው የማይደርስበት ገጠር ገባሁ››፡፡
 በርናርድ በሀገራችን በብቸኝነት የጉበት ካንሰርና ተዛማጅ በሸታዎች ቀዶ ሕክምና በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል እንዲሰጥ ያደረገ የሞያ ቁንጮ የነበረ ታላቅ ሰዉ መሆናኑን መመስከር አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን እጅግ በጣም ተገቢም ነዉ፡፡
 እስመ ትኅትና ይትረከብ ልዕልናእንዲል የሕክምናዉ ሊቅ እኔን እዩኝ ሳይል፣ አለሁ ብሎ ሳይፎክር ዕወቁኝ ብሎ ሳያዉጅ፣  ካልተወለደበት ወገን መካከል አገለገለ፡፡ እንደ ሀገሬዉ ባሕል እጅ ነሥቶ በባላገሩ ምርቃት ተመርቆ፣ ለድኾችና ረዳት ለሌላቸው ዋርካና መጠጊያ ሆነላቸዉ፡፡ በፍቱን እጁ ዳበሳቸዉ፡፡ ለወትሮው አመሰገኑት፡፡ በሄደበት በተገኘበት ቤት ያፈራዉን ሰንቀዉ እያመጡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ አሉት፡፡ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ፡፡ አንዲት ምስኪን እናት መጡ፡፡ እርሱም አከማቸው፡፡ ድህነታቸው ማግኘት ያለባቸውን ሕክምና አልከለከላቸውም፡፡ ከቅኖች ጋር አምላክ ይሠራልና ሴትዮዋ በበርናርድ ታክመው ዳኑ፡፡ ከቀናት በኋላ ሊያመሰግኑት ወደ ሆስፒታሉ ተመለሱ፡፡ መርቀው መርቀው ጨረሱና ከጉንፋቸው እጃቸውን ሰድደው አንድ ነገር አወጡ፡፡ ዐሥር ብ



አበው ሲመርቁ ‹‹ወይ መልካም ልጅ፣ ወይ መልካም ደቀ መዝሙር ይስጥህ›› ይላሉ፡፡ የሚረከብህ ማለታቸው ነው፡፡ ብዙ ታሪክ ሠሪዎች ታሪካቸውን የሚያስተላልፍላቸው አጥተው ሳናውቃቸው ቀርተናል፡፡ ዛሬ ታሪካቸውን ከፍ አድርገን የምንናገርላቸው ታላላቆቻችን ታሪካቸውን የሚጽፍ፣ የሚጠብቅና ለትውልድ የሚያስተላልፍ ያገኙትን ነው፡፡ ስማቸውን ሰምተን ታሪካቸው ያጣን፣ ሥራቸው ደርሶን ታሪካቸው የጠፋብን አያሌ ጀግኖች አሉን፡፡ አንዳንድ አባቶች እንዲያውም ሰው ሲያጡ ታሪካቸውንና ቅርሳቸውን ለወንዞችና ለተራሮች በአደራነት ሰጥተው ነበር፡፡ ይሄው በየዘመኑ እየተቆፈረ የሚወጣው ቅርስ መሬት አደራ የተቀበለችውን እያስረከበች ነው፡፡

በዘመናዊ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ጎልተው ከሚጠቀሱት ታላላቅ ሰዎች መካከል ሊቀ ሊቃውንት መሐሪ ትርፌ አንዱ ናቸው፡፡ የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ትርጓሜ(1948)፣ የሐዋርያት ሥራ ትርጓሜ፣ የሰባቱ መልእክታትን ትርጓሜ፣ የዮሐንስ ራእይን ትርጓሜ(1951) ያገኘነው በእርሳቸው ድካም ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ‹ርትዕት ፍኖት ዘባስልዮስ በባሕረ ጣና›(1948)፣ ‹መጽሐፈ በቁዔት ዘጾም ወዘበዓል›(1946)፣ ቃለ ምዕዳን(1948)፣ መዝገበ ሃይማኖት(1950) ይህንንም መጻሕፍቱ በመጀመሪያ ገጻቸው ‹ከሊቀ ሊቃውንት መሐሪ ትርፌ› በማለት ያስታውሱናል፡፡ በዚያ ዘመን  ጵጵስና ከሊቅነት በኋላ የሚመጣ መዓርግ ነበርና ቅዱስ ሲኖዶስ እኒህን ታላቅ ሊቅ ብጹዕ አቡነ ጴጥሮስ ‹የጎንደርና የበጌምድር ጳጳስ› ብሎ በሐምሌ 12 ቀን 1952 ዓም ሾማቸው፡፡
ብጹዕ አቡነ ጴጥሮስ ባገለገሉባቸው ቦታዎች በሦስት ነገሮች ይታወቃሉ፡፡ የመጀመሪያው ሁለገቡ ሊቅነታቸው ነው፡፡ የሀገር ቤቱን ትምህርት አንድ ሳያስቀሩ የተማሩ ናቸው፡፡ በተለይም ደግሞ በሐዲስ ኪዳን ትምህርታቸው የሚጠቀሱ ሊቅ ናቸው፡፡ ከሀገር ቤቱ ትምህርት ባሻገርም ወደ ግብጽ ተሻግረው ለሦስት ዓመታት ያህል ተምረው ተመልሰዋል፡፡ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት አንድን አባት ‹ሊቅ› የምትለው በሦስት ነገሮች ነው፡፡ በኦርቶዶክሳዊ ሕይወቱ፣ በኦርቶዶክሳዊ ትምህርቱ እና በኦርቶዶክሳዊ ድርሰቱ፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ይህን ከሚያሟሉት መካከል አንዱ ናቸው – አቡነ ጴጥሮስ (1901- 1961 ዓም)፡፡ 
አቡነ ጴጥሮስ የሚታወሱበት ሁለተኛው ነገር ያለማቋረጥ ዞረው በማስተማራቸው ነው፡፡ የጎንደር ከተማ ለእርሳቸው የሥራ ማዕከል እንጂ የመቀመጫ ከተማ አልነበረም፡፡ እንዲህ እንዳሁኑ መኪና ባልነበረበት ጊዜ እስከ ሱዳን ድንበር ድረስ በእግርና በበቅሎ ዞረው አጥቢያዎችን ጎብኝተዋል፣ አስተምረዋል፣ ችግሮችን በቅርበት ፈትተዋል፣ አጥምቀዋል፣ አብያተ ክርስቲያናትንም ተክለዋል፡፡ በዚህ አገልግሎታቸው የተነሣም እጅግ አስቸጋሪ በሚባሉ ቦታዎች የሚኖሩ ምእመናን ሳይቀር ያስታውሷቸዋል፡፡ 
በጎንደር ስለ አቡነ ጴጥሮስ ሐዋርያዊነት የሚነገር አንድ ትርክት አለ፡፡ ብጹዕ አባታችን ያለ ዕረፍት ከጋራ ጋራ፣ ከቆላ ቆላ ሲዘዋወሩ የተመለከቱ አንድ አባት ‹‹አባታችን ምነው ጥቂት ቢቀመጡ›› አሏቸው፡፡ አቡነ ጴጥሮስም ‹አይ አባታችን ሂዱ እንጂ መች ተቀመጡ ተባልን›› ብለው መለሱላቸው ይባላል፡፡  
የአቡነ ጴጥሮስ ሦስተኛው መታወሻቸው ለገዳማዊ ሕይወት የነበራቸው ፍቅር ነው፡፡ በተለይም ዐቢይ ጾምንና ጾመ ማርያምን ከከተማ ወጥተው በታላላቅ ገዳማት ማሳለፍ ይወዱ ነበር፡፡ በመጨረሻው ሕይወታቸውም ዕለተ ዕረፍታቸውን የተረዱት ለዐቢይ ጾም ሱባዔ በማኅበረ ሥላሴ ገዳም በነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡ እዚያ በሱባዔ ላይ እንዳሉ ዕረፍታቸው መድረሱን ዐወቁ፡፡ ወደ ጎንደር ተመልሰውም ሥራቸውን መልክ መልክ ማስያዝ ጀመሩ፡፡ በተለይም በየሀገሩ ሲዘዋወሩ ያሰባሰቧቸው ታሪካዊ ቅርሶች ለትውልድ ይተላለፉ ዘንድ ሁነኛ ሰው እንደሚያስፈልጋቸው ዐወቁ፡፡
አባ ሙሉ ሽታነህ በአቡነ ጴጥሮስ ዓይን የገቡት ያኔ ነበር፡፡ አባ ሙሉ አቡነ ቀሲሳቸው ናቸው፡፡ ዲቁናና ቅስና የሰጧቸው አቡነ ሚካኤል ሲሆኑ ቅኔና ቅዳሴን በሚገባ የተማሩ ሊቅ መነኮስ ናቸው፡፡ ደርቡሽ ያጠፋውን ኳንትቻ አርባዕቱ እንስሳ እንደገና ነፍስ የዘሩበት፣ አለፋ ወረዳ ያለቺውን ቼባ ማርያም እንደገና የገነቡ፣ በጉሙዝ አካባቢ ሐዋርያዊ ተልዕኳቸውን የፈጸሙ፣ የአንጋራ መድኃኔዓለምን ገዳም የእህል ችግር ለመፍታት በሬ በታንኳ ጭነው በመውሰድ ተአምር የሠሩ፣ የአቡን ቤት ገብርኤልን ባለ ታላቅ ሕንጻ አድርገው ካህናቱን ከልመና ያወጡ፣ የአባ ዝንግሪትን ድልድይ አስገንብተው ሕዝብን ያገናኙ፣ ከወጣት ጋር ወጣት፣ ከዐዋቂ ጋር ዐዋቂ ሆነው ለስብከተ ወንጌል የሚጣደፉ የጎንደር ፈርጥ ናቸው፡፡ 
 ይህንን የገመገሙት፣ በመንፈሰ ትንቢትም የተመለከቱት አቡነ ጴጥሮስ ታሪካዊ ቅርሶቻቸውን በአደራ ለአባ ሙሉ አስረከቧቸው፡፡ ይህንን አደራ አባ ሙሉ ለሃምሳ ዓመታት ጠብቀዋል፡፡ መሣሪያ ይዘው በኃይል ሲያስፈራሯቸው፣ ገንዘብ ይዘው በወርቅ ሲደልሏቸው፣ ሥልጣንን ተጠቅመው አውጣ አግባ ሲሏቸው፣ ተንኮል ተጠቅመው ለስርቆት ሲያሸምቁባቸው፤ እርሳቸው ግን ጸሎት ከጥበብ ተጠቅመው ከግማሽ ምእት በላይ ጠብቀዋል፡፡ ወርቅን በምናኔ ድል አድርገዋል፡፡ ቅርሶቹን አልባሌ አስመስለው በማስቀመጥ ሌቦችን አታለዋቸዋል፡፡ ቤታቸው የገባ ሰው እንኳን ቡትቶ የተከማቸ እንጂ ቅርስ የተቀመጠ መሆኑን አያውቅም ነበር፡፡ እርሳቸውም ሌላ ቦታ እንዳስቀመጡት ነበር የሚያወሩት፡፡ በሥልጣንና በኃይል የሚመጣባቸውንም በሱባዔ ያሳልፉታል፡፡     
አባ ሙሉ ዐቅማቸው እየደከመ፣ እድሜያቸው እየጨመረ ሄዷል፡፡ ሁለት ጊዜ በአገልግሎት ላይ ወድቀው ዛሬ በክራንች ነው የሚጓዙት፡፡ የዛሬ 23 ዓመት በጎንደር ሳገኛቸው የነበራቸው የሃይማኖት ጽናትና ለሥራ ያላቸው ፍቅር ግን መቼም የሚሞት አይመስልም፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን መርዳት፣ ወጣቶችን ማበረታታት፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚያስፈልጉ ግንባታዎችን በታማኝነትና በጥራት መሥራት፣ ገዳማትና ችግረኞች እንዲረዱ ማድረግ፣ የተጣሉትን ማስታረቅ፣ ዛሬም አልጋ ላይ ሆነው እንደገና ሊሠሩት የሚመኙት አገልግሎታቸው ነው፡፡ ሎሬት ጸጋየ ገብረ መድኅን በቴዎድሮስ ስንብት ላይ እንደገለጸው ‹ከሠሩት ነገር ይልቅ ያልሠሩት ይቆጫቸዋል››፡፡
አሥራ አንድ ሊቃነ ጳጳሳት በጎንደር ተፈራርቀዋል፡፡ አባ ሙሉ ግን ሳይቀየሩ ሁሉንም አገልግለዋል፡፡ የሁሉን ታሪክ ለግማሽ ምእተ ዓመት ሰብስበዋል፡፡ ወደ ፈጣሪያቸው ከመሄዳቸው በፊት ግን እነዚያን በተጋድሎ ያቆዩዋቸውን የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ንዋያተ ቅድሳት፣ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ቅርሶች ለትውልድ ማስረከብ ፈለጉ፡፡ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ኤልሳዕም ሐሳባቸውን ተቀብለው ለቅርሶቹ ማስቀመጫ ሙዝየም እንዲሠራ አደረጉ፡፡ ሙዝየሙም ጥቅምት 26 ቀን 2003 ዓም አስመረቁ፡፡ አባ ሙሉም ለሃምሳ ዓመታት የጠበቋቸውን ቅርሶችም ሕዝብና መንግሥት ባለበት፣ ቤተ ክህነትና ምእመናን በተገኙበት በይፋ ለትውልድ አስረከቡ፡፡
ታሪክ ሠሪ እንዲህ ያለ ታማኝ ታሪክ አሻጋሪ ሲያገኝ ምንኛ ዕድለኛ ያደርገዋል፡፡ አባ ሙሉን ያብዛልን፡፡    


መቼም ከጓደኞቹ ጋር ምሳ እንደመብላት የሚያስደስተው ነገር የለም፡፡ ከየትም ቦታ ተሯሩጦ ወደ ቀጠሮው ቦታ ይመጣል፡፡ ምንም እንኳን አንዳንድ ጊዜ ያቺ ያረጀች መኪናው ድንገት እየቆመች ብታስቸግረውም ቀጠሮውን ግን አይሰርዝም፡፡ አሁን የመኪና ማቆሚያ እየፈለገ ነው፡፡ አዲስ አበቤ ሁሉ ለሦስት ቀን ነነዌ ቅበላ ሀገሪቱን በቀንድ ከብት ሀብት አንደኛ ከመሆን ገፍትሮ ሊጥላት በየ ሥጋ ቤቱ ተጠቅጥቋል፡፡ መንገዱም አጥንት እንዳየ ጉንዳን በሚተራመሱ መኪኖች ተሞልቷል፡፡ እዚህ ነው ጓደኞቹ የቀጠሩት፡፡
በዋናው መንገድ በኩል ለመግባት ሞከረና ያለ ማስጠንቀቂያ የሚቆፈረው መንገድ ተዘግቶ አገኘው፡፡ እለፉም አትለፉም የማይል የአፈር ክምር መንገዱን ዘግቶታል፡፡ በታችኛው በኩል ዞረና መጣ፡፡ እንደ ደብረ ዕንቁ አንድ መውጫ ብቻ የቀረለት መንደር በግራ በቀኙ በቆሙት መኪኖች ተጣብቦ ጉርሻ እንዳነቀው ጉሮሮ ውጭ ነፍስ ግቢ ነፍስ ይላል፡፡ በወዲህና በወዲያ ምንም መቆሚያ አልተረፈም፡፡ 

‹በተወደደ ቁጥር ደንበኞቹን የሚጨመር ነገር ቢኖር ሥጋ ቤት ነው› ይላሉ አንድ በላተኛ የታጠቡትን እጃቸውን እያራገፉ ከሥጋ ቤት ወጥተው፡፡ ‹በዚህ የሥጋ ፍቅራችን የጾም ወቅት ባይኖር ምን ይውጠን ነበር› አሉ አብረዋቸው የወጡት ሰው፡፡ እርሱ ግን መሐል መንገድ ቆሞ ማቆሚያ ፍለጋ ያማትራል፡፡ ከኋላው ማለፊያ ያጡት መኪኖች እንደ ገጠር ሠርግ ጡሩንባቸውን ያንጣጡታል፡፡ ከፊት ለፊት ገበያቸው የቀረባቸው መኪና ጠባቂዎች ‹እባክህ እለፍ› ይሉታል፡፡ እርሱ ግን ‹አልበር እንዳሞራ ሰው አርጎ ፈጥሮኛል› እያለ ክንዱን መስኮት ላይ አስደግፎ ቆሟል፡፡
በመሐል ስልኩ ተደወለ፡፡ እኅቱ ነበረች፡፡ ‹‹ምጡ ሊጀምረኝ ነው መሰል ወገቤን እያመመኝ ነው› አለቺው፡፡ ‹‹አይዞሽ፣ በሦስተኛሽ ትጨነቂያለሽ እንዴ፤ ከፈለግሺኝ ደውዪልኝ›› አላትና ዘጋው፡፡ የእኅቱ ባለቤት ለሥራ ወደ ቻይና ሄዷል፡፡ አደራው ያለው እርሱ ጋ ነው፡፡ የጓደኞቹ ነገር ባይሆንበት አብሯት ቢሆን ነበር የሚመርጠው፡፡
አንድ የመኪና ጠባቂ መጣና ‹ቦታ ላሳይህ› አለው፡፡ ተከትሎት ነዳ፡፡ ወደ ውስጥ መግቢያ መንገድ ነው፡፡ ‹‹እዚህ ጋር አቁመው የሚገባ መኪና የለም› አለው፡፡ ስለሰለቸው ብቻ ወስዶ መንገዱን ዘጋና ገተረው፡፡ አንዳንድ ልጆች ‹እ ፍሬንድ ምነው መንገዱን ከረቸምሺውኮ› አሉት፡፡  ዝም ብሏቸው በሩን ቆልፎ ወደ ሥጋ ቤቱ ተጣደፈ፡፡ ማቆሙን አንጂ አቋቋሙን አላየውም፡፡ ከቀጠሮው ሠላሳ ደቂቃ አሳልፏል፡፡ ሥጋ ቤቱ ከጠጅ ቤት ጫጫታን ተውሶ ድብልቅልቁ ወጥቷል፡፡ ማን ምን እንደሚል አይሰማም፡፡ የሚሰማው የቢላዋ ፍጭት ብቻ ነው፡፡ ሁሉም ይጮኻል፣ ሁሉም ይሰማል፡፡ ሁሉም ግን አያዳምጥም፡፡  
በዓይኑ እያማተረ ፈለጋቸው፡፡ እንደ ሞባይል ሠሪ ሁሉም አጎንብሰው ያስነኩታል፡፡ በቅርጻቸው እንጂ በመልካቸው ለመለየት አልቻለም ነበር፡፡የመጀመሪያው ትእዛዝ ተጋምሶ ደረሰ፡፡ ከአራት አቅጣጫ በመጣለት ጉርሻም ከቡድኑ ተቀላቀለ፡፡
                            ***                    ****                    ***             ***            ***
እኅቱ ምጧ እየተፋፋመ መጣ፡፡ ምን እንደሆነ እርሷም አታውቀውም እንጂ ይኼኛውን እርግዝና ቀድሞም ፈርታዋለች፡፡ እንዳመማት ነው የከረመው፡፡ የበካር እርግዝና ይመስላል፡፡ ለወንድሟ ደወለችለት፡፡ ስልኩ ይጠራል፣ ግን አይነሣም፡፡ እየደጋገመች ደወለች፡፡ ለውጥ አልነበረውም፡፡ ሌላ መኪና ያለው ሰው ደግሞ አታውቅም፡፡ የመጨረሻ አማራጯ ይከታተላት የነበረው ሐኪም የነገራትን የስልክ ቁጥር መጠቀም ነበር፡፡ ወደ ሆስፒታሉ ደወለች፡፡ ስልኩን ያነሣው ሰው አምቡላንሱን በአስቸኳይ እንደሚልክላት ቃል ገብቶ አድራሻዋን ወሰደ፡፡
ወገቧን እያመማት፣ ድካምም እየተሰማት አምቡላንሱን መጠበቅ ጀመረች፡፡ ዐሥር፣ ዐሥራ አምስት፣ ሃያ፣ ሠላሳ፣ ዐርባ ደቂቃዎች አለፉ፡፡ መልሳ ወደ አምቡላንሱ ደወለች፡፡ ያነሳው ሰውዬ ‹‹ይቅርታ አንድ ሰው መኪና አቁሞ መንገዱን ስለዘጋብን ነው፣ ትንሽ ታገሽን› አላት፡፡ ምን አማራጭ አለኝ ብላ ጠበቀች፡፡ ሕመሟ ሲበረታ ታክሲ እንዲጠሩላት ጎረቤቷን አስጠራቻቸው፡፡ ቤታቸው ከመንገድ ገባ ያለ በመሆኑ ዋናው መንገድ ድረስ በእግር መጓዝ ነበረባቸው፡፡
እርሳቸው ወደ ዋናው መንገድ ሲያዘግሙ እርሷም ወደ ድካምና ሽንፈት እያዘገመች ነበረች፡፡ መንገዱ ዳር ሲወጡ ሁሉም ባለ ታክሲዎች ለቅበላው ሥጋ ቤት ከትመዋል መሰል ትንንሾ ታክሲዎች የሉም፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ በቅበላ፣ በገብርኤል፣ በአርሴናልና ማንቸስተር የጨዋታ ቀናት ታክሲ ማግኘት ሕልም ነው፡፡ ትልልቆቹም እየሞሉ በኩራት ያልፋሉ፡፡ መቼም ትልልቅ ታክሲዎች ባዷቸውን ሲሆኑ የሚደርስባቸውን የመጠበቅ መከራ የሚበቀሉት ሲሞሉ  በኩራት ገልምጠው በማለፍ ይመስላል፡፡ እንደ መቆም ይሉና እንቁልልጭ ብለው እንደ መሸምጠጥ ይላሉ፡፡  
ጎረቤቷ ሲዘገዩባት ያለ የሌለ ኃይሏን አስተባብራ ወደ ሆስፒታሉ ደወለች፡፡ ስልኩን ያነሣው ሰውዬ ‹‹እባክሽ አንድ ምን እንደምለው የማላውቅ ሰው መንገድ ዘግቶ ጠፍቷል፡፡ እዚያ ሥጋ ቤት ሳይገባ አልቀረም፡፡ ሰው ልከን በታርጋ ቁጥሩ ብንፈልገውም ጫጫታው ነው መሰል ሊሰማን አልቻለም፡፡ በወዲያ በኩል ያለው መንገድ ደግሞ ተቆፍሯል፡፡ ከቻልሽ ሌላ መኪና ይዘሽ ነዪ›› አላት፡፡ ተስፋ ወደ መቁረጥ ልትገባ ስትል ጎረቤቷ ከቅበላ የተረፈች ታክሲ ይዘው መጡና ከቤት ሠራተኛዋና ከሹፌሩ ጋር አፋፍሰው ይዘዋት በረሩ፡፡
የሥጋ ቤቱ መንገድ እንደተጨናነቀ ነው፡፡ ቅበላውን ተቀብለው፣ ጾሙንም በሙዳ ሥጋ ይዘው የሚወጡት ተመጋቢዎች አልፋለሁ አታልፍም እየተነታረኩ ነው፡፡ የታክሲው ሾፌር ‹‹ኧረ እባካችሁ ወላድ ይዘን ነው›› እያለ በመስኮቱ በኩል ይለምናል፡፡ አንዳንዶቹ ጩኸቱን በመከራ ሰምተው ለመጠጋት ይሞክራሉ፡፡ ይገጩናል ብለው የፈሩ ሌሎች ደግሞ በጡሩንባ ድምጽ ያባርሯቸዋል፡፡ የሞተ አህያ ለመብላት አሞሮች የሚያሳዩት ትርዒት ይመስል ነበር፡፡
እንደምንም ብሎ የጎንና ጎን መመልከቻ መስተዋቱን እያጠፈ፣ በዔሊ ፍጥነት የውስጥ መንገዱን አለፈውና ወደ ሆስፒታሉ ለመግባት ወደ ግራ ሲታጠፍ መንገዱ ተዘግቷል፡፡ ከወዲያ ማዶ አንድ አምቡላንስ ቆሟል፡፡ ነጭ ገዋን የለበሱ የሆስፒታሉ ሰዎች ወዲያና ወዲህ ይራወጣሉ፡፡ ፖሊሶች መኪና አቋሚውን ቢያገኙት ሊቦጫጭቁት በሚደርስ ንዴት ውስጥ ናቸው፡፡ የትራፊክ ፖሊሶች ታርጋ ይፈታሉ፡፡ የታክሲው ሾፌር ደግሞ ‹አሳልፉኝ› እያለ ይጮኻል፡፡
አንድ አልፎ ሂያጅ ሽማግሌ ግን ግራ ቀኙን ሲያዳምጡና ሲቃኙ ቆዩና ‹‹ሰው ማለትኮ ለሚፈጽመው ነገር አንዳች ምክንያት ያለው፣ የሚሠራው ነገር ሊያስከትል የሚችለውን ነገር ቀድሞ አስቦ የሚሠራ ፍጡር ማለት ነው፡፡ የሚያደርጉት ነገር ምን ሊያስከትል እንደሚችል የማያስቡ፣ በዚህም የተነሣ ኃላፊነት ሊሰማቸው የማይችል እንስሳት ብቻ ናቸው፡፡ እስካሁን እንደ ሰው የሚኖሩና የሚያስቡ እንስሳት አልተገኙም፤ እንደ እንስሳት የሚኖሩና የሚያስቡ ሰዎች ግን በብዛት አሉ፡፡ ኃላፊነት ሁለት ዓይነት ነው፤ የሹመት ኃላፊነት አለ፡፡ ለሥራና ለአገልግሎት የሚሰጥ፡፡ ዋናው ግን እርሱ አይደለም፡፡ ዋናው ሁለተኛው ነው፡፡ ሰው በመሆን ምክንያት ብቻ የሚመጣ ኃላፊነት፡፡ ሰው ስለሆንክ ብቻ ነገሮችን ሁሉ በኃላፊነት ስሜት እንድታከናውን የሚያስገድድህ የሰውነት ኃላፊነት አለብህ፡፡አንድን ፈረስ ከነ ጋሪው ብትለቅቀው ልክ እንደዚህ ሰውዬ አንዱ ቦታ ላይ ይቆማል፡፡ የቆመበት ምክንያት ሣር ስላገኘ ብቻ ነው፣ ወይም ጥላ፡፡ አለቀ በቃ፡፡ በመቆሙ የሚያመጣውን ነገር እንዲያስብ አይጠበቅበትም፡፡ ኃላፊነት የማይሰማቸው ሰዎችም እንደዚህ ፈረስ ናቸው፡፡›› አሉና እየተራገሙ ሄዱ፡፡
ሁለት ነርሶች መጡና እርጉዟን ተሸከሟት፡፡ ግርግሩን ሲያደምቅ የነበረው ሁሉ ከፊት ከኋላ ከቀኝ ከግራ ደግፎ መንገድ ዘግቶ የቆመውን መኪና አሻገራት፡፡ አምቡላንሱ እንደምንም ፊቱን መልሶ ይዟት ወደ ሆስፒታሉ ሸመጠጠ፡፡
መንገድ ዘግቶ በቆመው መኪና ዙሪያ ፖሊሱ፣ መኪና ጠባቂው፣ በልቶ ተመላሹ፣ ወሬ ጠምቶት የቆመው አላፊ አግዳሚ ወጉን ጮክ እያለ ይሰልቃል፡፤ አንዳንዱ ያወግዛል፤ አንዳንዱ ባለ መኪናው ሲመጣ ሊፈጠር የሚችለውን እየገመተ ይተነትናል፤ሌላው ደግሞ መወሰድ ስላለበት ርምጃ ሐሳብ ይሰጣል፤የባሰበትም ‹አይ አበሻ› እያለ ራሱን ጨምሮ ይረግማል፡፡ በዚህ መሐል የታጠቡበትን እጅ እያፍተለተሉ አንድ አምስት ጎልማሶች ጮክ ብለው እያወሩ መጡ፡፡ አንዱ ከመካከላቸው ነጠል ብሎ ሰዎቹ ወደተሰበሰቡበት አቀና፡፡ የተሰበሰቡት የርሱን መኪና ከበው መሆኑን፣ ፖሊሶቹ መቁነጥነጣቸውን ሲያይ አንዳች ክፉ ነገር ሸተተው፡፡
‹‹አንተ ነህ ባለ መኪናው›› አለ የትራፊክ ፖሊሱ፡፡
‹‹አዎ›› ሲለው ምን ሊመጣ ይሆን ብሎ እያሰበ ነበር፡፡
‹‹መንጃ ፈቃድህን ከመንገድ ላይ ነው እንዴ ያገኘኸው›› አለው ፖሊሱ፡፡
ባለ መኪናው ዝም አለ፡፡
ከግራ ከቀኝ የስድብና የርግማን መዓት ይወረወርበታል፡፡ ጓደኞቹ ሁኔታውን አይተው መጡ፡፡ 
‹‹በል አስነሣና ወደ ፖሊስ ጣቢያ›› አለው ፖሊሱ፡፡ ጓደኞቹ የተፈጠረውን ነገር ከከበቡት ሰዎች እየጠያየቁ ነው፡፡ መኪናውን ለማስነሣት በሩን ከፈተ፡፡ ጥሎት የሄደውን ስልኩን አንሥቶ ሲያየው ከሃያ በላይ አምላጭ ስልክ አለው፡፡ ፖሊሱ እያጣደፈው እንደምንም ያመለጡትን ስልኮች አየ፤ አብዛኛው የእኅቱ ነው፡፡ ግራ ገባው፡፡
‹‹አንዴ ልደውል›› አለው ፖሊሱን
‹‹ባክህ ወደ ጣቢያ ሂድ፤ ስንት ችግር እንደፈጠርክ እዚያ እንነግርሃለን›› አለው ፖሊሱ፡፡
‹‹እኅቴ ስለሆነች ነው›› አለ፡፡
‹‹እዚህ መኪናውን ገትረህ የስንቱን እኅት ስታስለቅስ ነው የቆየኸው፤ ባክህ ንዳው›› አለ ፖሊሱ፡፡
ቁልፉን ተረክ አድርጎ አስነሣው፡፡ ልቡ ግን በድንጋጤና በሥጋት እንደ ጥምቀት ከበሮ ይመታል፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ሲደርስ ፖሊሱ ቁጣው አልበረደም ነበር፡፡
‹‹እንዴት አንተ የሆስፒታል መንገድ ትዘጋለህ?›› አለው በንዴት
‹‹አላወቅኩም ነበር›› ብሎ መለሰለት፡፡
‹‹እንዴት ነው የማታውቀው፤ ምልክት ማየት አቅቶህ ነው››
‹‹ስለቸኮልኩ ልጆቹ አቁመው ሲሉኝ አቆምኩት››
ጣቢያ ያሉት ሁሉ ከራሱ ውጭ ግድ የሌለው፣ ለሌላው የማያስብ፣ ሥርዓት የለሽ፣ ማን አለብኝ ባይ ጎረምሳ አድርገው ገመቱት፡፡ ለማስረዳት ብዙም አልጣረም፡፡ ልቡ ከእኅቱ ጋር ነበር፡፡ ጣጣውን በግማሽ ሰዓት ውስጥ ጨርሶ ቅጣቱን በቀሪው ግማሽ ሰዓት ተቀጥቶ፣ ወደ እኅቱ ደወለ፡፡ አንድ ሴትዮ አነሡና ‹‹ሐኪሞቹ አትግቡ ስላሉ ሰው አታናግርም›› አሉት፡፡ ጎረቤቷ ነበሩ፡፡
‹‹የት ነው ያለቺው›› ሲል ጠየቃቸው፡፡ ቦታውን ሲነግሩት እዚያው አካባቢ ነበር፡፡ ከፖሊስ ጣቢያ በር ላይ የቆመውን ፖሊስ ሲጠይቀው ‹‹ቅድም ያንን ሆስፒታል ዘግተህ አይደል እንዴ የቆምከው›› አለው፡፡ ሌላ ነገር ከመከሰቱ በፊት አመስግኖት ወጣ፡፡ ልቡ ግም ገጭ ይላል፡፡ መኪና አቁሞ በነበረበት መንገድ በኩል ወደ ሆስፒታሉ ሲገባ መንገደኞቹ በሙሉ መኪናውን የለዩት ይመስል በክፉ ዓይን ነበር የሚያዩት፡፡ መኪናውን ግቢው ውስጥ ሲያቆም ብዙዎች ይጠቋቆሙበታል፡፡ ወደ ሕንፃው ገባና የእኅቱን ስም ጠርቶ የአልጋ ክፍሏን ጠየቀ፡፡ ከመስኮቱ ኋላ ያለቺው ልጅ ቁጥሩን ነገረቺውና ‹‹የበደልካትን ልትክሳት ነው እንዴ›› አለቺው፡፡
‹‹ለምን እክሳታለሁ›› አለ ገርሞት
‹‹አንተ አይደለህ እንዴ መንገድ ዘግተህ አምቡላንስ የከለከልካት›› አለቺው በዓይኗ እየገረፈች
‹ዋት?› አለና ወደ ደረጃው በሩጫ ወጣ፡፡ ልቡ ከደረቱ ውጭ ያለ መሰለውና በእጁ ዳሰሰው፡፡
የሠፈሩ ሰው በሩ ላይ ከብቧል፡፡ ማንም በበጎ አልተቀበለውም፡፡
ጎረቤቷን ሴትዮ ፈለገና ‹‹እንዴት ናት›› አላቸው
‹‹ሐኪሞቹ ደኅና ናት ብለዋል›› አሉት፡፡
‹‹ምነው ባሰባት እንዴ››
ጎረቤቷ በኀዘን መሬት መሬት እያዩ ‹‹ምን አንድ የተረገመ ሰውዬ የሆስፒታሉ መንገድ ላይ መኪናውን አቁሞ አምቡላንሱስ በየት ይምጣ፣ እርሷን በታክሲ ስናመጣት በየት ትግባ፡፡ በዚህ የተነሣ አደጋ ውስጥ ልትወድቅብን ነበር፤ መድኃኔዓለም አተረፈልን፤ አንተም ስልክህን አታነሣውም›› አሉና ቀና ሲሉ  እርሱ የለም፡፡ የመጀመሪያውን ርግማን እንደሰማ አእምሮውን ስቶ ተንሸራትቶ ወድቋል፡፡


ማክሰኞ ለም ሆቴል አካባቢ ለመንገድ የተቆፈረ ገደል ውስጥ የገባው መኪና(ፎቶ ፡- ጽላት ጌታቸው)

ከግንባታዎች ጋር ተያይዞ እየደረሰ ያለው አደጋ አሳዛኝ እየሆነ ነው፡፡ ይኼ አደጋ በሦስት ነገሮች ምክንያት እየደረሰ ያለ ይመስለኛል፡፡ የመጀመሪያው ግንባታዎች ሲከናወኑ ተገቢ የሆነው ቅድመ፣ጊዜና ድኅረ ግንባታ ጥንቃቄ ስለማይወሰድ ነው፡፡ ታላላቅ ክሬኖች አገር ደርምሶ የሚሄድ ቋጥኝ አንጠልጥለው እየታዩ፣ በሥራቸው ሰውና መኪና እንዲያልፍ ይደረጋል፡፡ ለግንባታ ሠራተኞች በቂ የሆነ የአደጋ መከላከያ ሥልጠናና መሣሪያ አይሰጣቸውም፡፡ አማራጭ መንገዶችና የእንቅስቃሴ ቦታዎች ቀድመው ስለማይዘጋጁ ግንባታና ኑሮ ጎን ለጎን ይካሄዳል፡፡ መታጠር ያለባቸው ሳይታጠሩ፣ መሸፈን ያለባቸው ሳይሸፈኑ፣ መከደን ያለባቸው ጉድጓዶች ሳይከደኑ፣ ምልክት መደረግ ያለባቸው ቦታዎች ላይ ሳይደረጉ ግንባታዎች ይከናወናሉ፡፡ በዚህም የተነሣ በተገቢ ጥንቃቄ ሊተርፉ ይችሉ የነበሩ ሕይወቶች ይቀጠፋሉ፣ አካል ይጎድላል፣ ንብረት ይወድማል፡፡

ግንባታዎች በመንደሮች መካከል ሲከናወኑ አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያንና ሕጻናት የሌሉበት መንደር ይመስላል፡፡ በየቦታው ጉድጓዱ አፉን ከፍቶ ማየት የተሳናቸውን ሊውጥ አሰፍስፏል፤ አረጋውያንን ‹እስኪ ትዘልና› ይላል፡፡ ሕጻናትን ዋኝተው እንዲያልፉበት ይጋብዛል፡፡ በዊልቼር ለሚጓዙ፣ በከዘራ ለሚራመዱ፣ በክራንች ለሚታገዙ ቦታ የለውም፡፡ 
አንድ ግንባታ ከመከናወኑ በፊት የሚገነባው አካል በሚያስገባው የጨረታ ሰነድ ውስጥ የቅድመ ጥንቃቄ አሠራሮቹ አብረው እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ግን ለጨረታ ሰነድ ማሟያነት ይውላሉ እንጂ ተከታትሎ የሚያስፈጽማቸው አያገኙም፡፡ በእነዚህ የጨረታ ሰነዶች ላይ ለግንባታ ሠራተኞችና ለነዋሪዎች ሊደረጉ የሚገባቸው ጥንቃቄዎች ይገለጣሉ፡፡ ነገር ግን የሚቀሩት መደርደሪያ ላይ ነው፡፡ አንድን የግንባታ አካባቢ ገንቢው ሲረከብ የርክክብ ሥነ ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ከዚያ በኋላ አካባቢው የገንቢው አካባቢ ነው፤ በዚያ አካባቢ ለሚደርሰው ጉዳትም ተጠያቂው እርሱ ነው፡፡ ኢንሹራንስ እንዲገባ የሚደረገውም ለዚህ ነው፡፡ ነገር ግን አስፈጻሚው አካል ተከታትሎ ለማስፈጸምና በሕጉ እንዲመራ ለማድረግ የዐቅምም የሙስናም ችግር ያለ ይመስላል፡፡ 
አንድ ግንባታ ሲከናወን የአደጋ መከላከያ ወጭ ከግምት መግባት አለበት፡፡ በአንድ በኩል ከግንባታው ጋር ቀጥታ ስለማይያያዝ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ወጭው ከፍተኛ ስለሚሆን ተጫራቾች የአደጋ መከላከያ ወጭን ይተውታል፡፡ ተቆጣጣሪዎችም በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ያልፉታል፡፡ የመንግሥት ፕሮጀክቶች ሲሆኑ ደግሞ እንደ ወጭ መቀነሻ አማራጭ ይወሰዳሉ፡፡ በዚህ ምክንያትም ጆሮ ጭው የሚያደርግ አደጋ በየቀኑ መስማት የየዕለት ሰበር ዜናችን ሆኗል፡፡ ለዜጎች የሚገነባ ግንባታ ዜጎችን ያለ ፍላጎታቸው ይቀጥፋል፡፡ 
ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ያሉን ነባር መንገዶችና ሕንጻዎች ያረጁ፣ በሚገባ ያልተገነቡና አሁን የሚደረጉ ግንባታዎች ለሚያስከትሉት ጫና ቀድመው ያልተዘጋጁ መሆናቸው ነው፡፡ በጣልያን ዘመን በተሠሩ ቤቶች ጎን፣ የጥገና ጊዜያቸውን ጠብቀው በማይጠገኑ ሕንጻዎች አጠገብ፣ እንደነገሩ ሲጠጋገን በኖረ ድልድይ ዳር፣ የፍሳሽ ማስወገጃዎች ተጠርገውና ተስተካክለው በማያውቁበት ከተማ ውስጥ ነው ግንባታዎች እየተከናወኑ የሚገኙት፡፡ መሬት አርዕድ አንቀጥቅጥ ማሽኖች፣ አስገምጋሚ ዶዘሮች፣ ሕንጻ ነቅንቅ ቁፋሮዎች፣ ጆሮ በጥስ የመሣሪያ ጩኸቶች፣ ግድግዳ ሰንጥቅ የድንጋይ ናዳዎች ናቸው በየአካባቢዎቻችን እየተከናወኑ ያሉት፡፡ ቤቶቻችንና ሕንጻዎቻችን፣ መንገዶቻችንና ድልድዮቻችን ለእነዚህ አዳዲስ ክስተቶች ታስበው የተዘጋጁ አይደሉም፡፡ መዓት ነው የወረደባቸው፡፡ አርማጌዶን የደረሰ እስኪመስል ድረስ አካባቢያችን ይደረመሳል፣ ይገመሳል፣ ይንቀጠቀጣል፣ በየቀኑ ይለዋወጣል፡፡ የኛ ሠፈር ግን ለዚህ አልተዘጋጀችም፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የተደረጉ ተደጋጋሚ ጥናቶች አብዛኞቹ ነባር ቤቶች ከደረጃ በታች የሆኑ ወይም የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ያለፈባቸው መሆናቸውን ገልጠዋል፡፡ ይህ እየታወቀ ግን ግንባታዎች ሲከናወኑ ሊደረመስ የሚችል ቤት፣ ሕንጻ ወይም ግንብ፣ ሊናድ የሚችል ገደል፣ ሊወድቅ የሚችል ድልድይ፣ ሊሰምጥ የሚችል ጉድባ፣ ሊሰነጠቅ የሚችል ግድግዳ መኖር አለመኖሩ ተለይቶ ጥንቃቄ ሲደረግ አይታይም፡፡ አንድ ‹ዳምጠው› መኪና ሲያልፍ ቤቶቻችን ጎንደርኛ እየጨፈሩ ያጅቡታል፡፡ ቆይተውም በዘፈኑ ብዛት ልባቸው ጠፍቶ በዚያው ይወድቃሉ፡፡    
 

በባቡር ግንባታ ጊዜ በተደረመሰ ግንብ የሞተቺው ወጣት የቀብር ሥነ ሥርዓት(ፎቶ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ)

ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ የማሳወቅ ግዴታችንን ስለማንወጣ ነው፡፡ መንደር ለውጥ፣ ምድር አንቀጥቅጥ ግንባታ ሲከናወን ኅብረተሰቡ(በተለይም በቀጥታ ጉዳዩ የሚመለከተው የአካባቢው ነዋሪ) በበቂ ሁኔታ እንዲያውቀውና የራሱን ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ኃላፊነቱን የሚወጣ አካል ያለ አይመስልም፡፡ በመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ከመስጠት ያለፈ ግዴታ እንዳለም ተዘንግቷል፡፡ በሌላው ዓለም አካባቢን የሚለውጥ ግንባታ ሲደረግ የሠፈሩ ሰው ዝርዝር ጉዳዩ ተጽፎ በየቤቱ ይሰጠዋል፡፡ ተሰብስቦም እንዲወያይ ይደረጋል፡፡ ሐሳቡን ያቀርባል፡፡ ግንባታው ለነዋሪውም ሆነ ለገንቢው ችግር በማይፈጥር መንገድ እንዲከናወን የጋራ መግባባት ላይ እንዲደረስ ይሞከራል፡፡ ማኅበረሰቡ ሊያከናውናቸው የሚገቡ ጥንቃቄዎች ይነገሩታል፡፡ ተቃውሞ ካለውም በምክንያት እንዲያስረዳ ይደረጋል፡፡ አሳማኝ ከሆነም ፕሮጀክቱ ይስተካከላል፡፡ እንዲያም ሲል ይቀራል፤ ፕሮጀክቱ የሚሠራው ለእርሱ ነዋ፡፡ በዚህ የተነሣም ዕድገት እሴት(asset) እንጂ ዕዳ(liability) አይሆንበትም፡፡ 
ባለፈው ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በድሬዳዋ ከተማ ከሀገር ሽማግሌዎች ጋር በተወያዩ ጊዜ የአካባቢው ሽማግሌዎች ያቀረቡት ጥያቄ እዚህ ላይ ሊጠቀስ ግድ ይላል፡፡ ከባቡሩ መንገድ ጎን ለእግረኛ የተሠራው ድልድይ ክፍት ድልድይ አይደለም፡፡ ከላይ ጣራ መሰል ነገር አለው፡፡ ነገር ግን ይኼ ድልድይ ሲሠራ ግመሎችን እንዲያሳልፍ ሆኖ አልተሠራም፡፡ ለምን? አሉ ሽማግሌዎቹ፡፡ በወቅቱ ሌላ ምላሽ ቢሰጣቸውም ምክንያቱ ግን እነርሱን ያላሳተፈና ሐሳብ ያልሰጡበት ግንባታ መከናወኑ ነው፡፡ አያውቁም ተብሎ ነው የሚታመነው፡፡ ያነሡት ሐሳብ ግን ሕዝብን የማያሳትፍና ይሁንታ ያልሰጠበት ሥራ ሁሉ ከሪፖርት ያለፈ ዋጋ እንደሌለው ያሳየ ነው፡፡ ድልድዩ ችግራቸውን ከመፍታት ይልቅ ራሱ ችግር ነው የሆነባቸው፡፡
መኖሪያ ማለት ጣራና ግድግዳ ብቻ አይደለም፡፡ አካባቢም ጭምር ነው፡፡ ለብዙ ዘመናት የኖረበት ወይም እኖርበታለሁ ብሎ የሚያስበው አካባቢ በአንድ ማለዳ ተለውጦ ሲጠብቀው፣ ለነዋሪው ሕመም እንጂ ደስታ አይፈጥርለትም፡፡ አስቀድሞ የማወቅ፣ ለሚመጣው ለውጥ የመዘጋጀት፣ ለውጡ ለሚያስከትለው አሉታዊ ነገር ጥንቃቄ የማድረግ፣ ለውጡን በሚችለው ሁሉ የማገዝና ለውጡም ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝን ከሆነ እስከማስቀረት የሚደርስ መብት ሊኖረው ይገባል፡፡ አንድ ነገር ‹መልካም ነው› ማለትና ‹ተቀባይነት አለው› ማለት ይለያያሉ፡፡ መልካም ነገሮች መልካም ሆነው እንዳይቀጥሉ ከሚያደርጓቸው ምክንያቶች አንዱ የሕዝብ ተቀባይነት ማጣት ነው፡፡ የመንግሥት አንዱ ኃላፊነት መልካም ነው ብሎ ያመጣው ነገር ሕዝባዊ ተቀባይነት እንዲኖረው የመሥራት ግዴታ ነው፡፡ የማስረዳት፣ የማሳወቅና የሕዝቡን ሐሳብ የመቀበል ግዴታ፡፡ 
ግንባታዎች በሚከናወኑበት አካባቢ መረጃ ሰጭ ምልክቶች የሉም ማለት ይቻላል፡፡ ምን እየተከናወነ ነው? ለተዘጋው መንገድ አማራጩ ምንድን ነው? መኪኖች በየት ይታጠፉ? እግረኞችስ በየት ይለፉ? ምን ጥንቃቄ ይደረግ? የሚገነባው ግንባታ አካባቢውን እንዴት ይቀይረዋል? ከፍታው፣ ጥልቀቱ፣ ስፋቱ ምን ያህል ነው? ገደል ነው ሜዳ? ውኃማ ነው ደረቅ? ዋሻ ነው ግልጥ? ከላይ የሚወድቅ ነገር አለ ወይስ የለም? በአካባቢው መኪና ማቆም ይቻላል አይቻልም? ከስንት ሰዓት እስከ ስንት ሰዓት ግንባታው ይከናወናል? ቄሱም ዝም መጽሐፉም ዝም ነው፡፡ ‹‹ምን አስቸኮላችሁ፤ እዚያው ሲደርስባችሁ ታውቁታላችሁ›› የተባለ ይመስላል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ አደጋ የሚያስከትሉ ነገሮችን እንኳን የሚያመለክት ምልክት በሚገባ አይኖርም፡፡ በዚህ ምክንያት ገደል የሚገቡ መኪኖችንና ሰዎችን እያየን ነው፡፡  
በሰሞኑ እንኳን ከግንባታ ጋር የተያያዙ አሰቃቂ ዜናዎችን እየሰማን ያለነው እነዚህ ሦስት ነገሮች ስለተዘነጉ ይመስለኛል፡፡ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አስቀድሞ የሚነግራቸው በማጣታቸው የትምህርት ቤት አጥር ሥር ተቀምጠው የነበሩ ተማሪዎች በመንገድ ግንባታ ንዝረት ግንቡ ተደርምሶ መዓት ወረደባቸው፡፡ ሰኞ ዕለት ደግሞ አፍንጮ በር አካባቢ በአሮጌ ማዕድ ቤት ውስጥ ሲሠሩ የነበሩ አዳጊ ልጆች በአካባቢያቸው እየተካሄደ ያለው ነገር ምን እንደሚያስከትል ስላልተነገራቸው አንዷ ለሞት አንዷም ለጉዳት ተዳረጉ፡፡ ለምን? አሁን እየገነባን ያለነው ግንባታኮ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው ግንባታ አይደለም፡፡ ከአኩስም ዘመን ተነሥተን እንኳን ብናሰላ ከሁለት ሺ ዘመን በላይ በግንባታ ላይ አሳልፈናል፡፡ እንዴት እንደ አዲስ ገንቢ ስሕተቱ የግንባታውን ያህል ይሆናል? በዓለም ላይ እኛ የመጀመሪያዎቹ ገንቢዎች አይደለንም፡፡ ከቀደሙት ልንማራቸው፤ ተምረንም ልንተገብራቸው የሚገቡ ነገሮች ሞልተው ተርፈው እንዴት በ21ኛው መክዘ የ1ኛው (ቅልክ) ስሕተት ይሠራል?
እንደ እኔ የሚመለከታቸው አካላት እነዚህን ነገሮች ቢያደርጉ አደጋውን መቀነስ፣ ከዚያም አልፎ ማስቀረት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
1.  የሚቻለው ቅድመ፣ ጊዜና ድኅረ ግንባታ ጥንቃቄዎችን ማድረግ፡፡ ወጭ ለመቆጠብ ወይም ደግሞ ጉዳዩን ለማፋጠን ሲባል የጥንቃቄ ነገሮችን መዝለልና መቀነስ ቀርቶ፣ ልማዳዊ በሆነው መንገድ መሥራት አብቅቶ፣ አደጋው ቀድሞ ከመከላከል ይልቅ ለአደጋው ዜና አዘጋገብ መጨነቅ ተወግዶ የሚቻለው ጥንቃቄ ሁሉ መደረግ አለበት፡፡ ‹ማስተዋል ይጋርድሃል፣ ጥንቃቄም ይጠብቅሃል› እንዲል መጽሐፉ፡፡ 
2.  የአካባቢው ነዋሪና ተጠቃሚ ስለ ግንባታው እንዲያውቅ፣ ዐውቆም እንዲዘጋጅ፣ ሐሳብም እንዲሰጥ በዝርዝር ማወያየት፣ መረጃውን በየቤቱ መስጠት፤ ሐሳቡን መቀበልና ተግባቦትን መፍጠር
3.  በቂና ግልጽ ምልክቶችን በአካባቢው መጠቀም፡፡ ዝርዝር መረጃ የሚሰጡና አደጋዎችን የሚያመላክቱ ምልክቶችን በአካባቢው ሕዝብ ሊመለከት በሚችልበት ቦታ ማስቀመጥ
4.  ማኅበረሰቡ ጉዳዩን እንዲከታተል ማኅበረሰብ ዐቀፍ ኮሚቴ ማቋቋምና ችግሮች ከመድረሳቸው በፊት ከነዋሪውና ከሚመለከታቸው ጋር እንዲሠራ ማድረግ
5.  ግንባታዎቹ እየተከናወኑ ያሉት በሕዝብ መካከል ነውና የሕዝቡን እንቅስቃሴ ግምት ውስጥ እንዲያስገቡ ከዲዛይኑ ጀምሮ መሥራት፡፡ ከተማዋን በባቡር ምክንያት በአራት ክፍለ ከተማ ከፍለን ያንንም በአጥር ከልለን፣ ዘላችሁ አታቋርጡ ማለት በጆሮ ግንድ በኩል አዙራችሁ ጉረሱ እንደማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ከመነሻው ምን ያህል ተጉዞ ነው መንገድ ማግኘት ያለበት?የሚለው ነገር የታወቀ ዓለም ዐቀፍ ደረጃ አለው፡፡ ሰው በጠባዩ አጭር መንገድ ይፈልጋል፡፡ ይህንን የሰው ጠባይ በአጥር ብቻ ለማስቀረት ከመታገል ከዲዛይኑ ጀምሮ ዓለም ዐቀፍ ደረጃዎችን ተጠቅሞ ማሰቡ አደጋዎችን ያስቀራቸዋል፡፡
6.  ብዙ ጊዜ ዓመታት በዓላቸውን ሲያከብሩ ወይም ጠቅላላ ጉባኤ ሲያደርጉ ብቻ በመገናኛ ብዙኃን ስማቸውን የምንሰማቸው የሞያ ማኅበራት(የአርክቴክቶች፣ የሲቪል መሐንዲሶች፣ የሕንጻ ተቋራጮች፣ ወዘተ) ተገቢው ቦታና ሥልጣን ተሰጥቷቸው የግንባታዎችን ሂደት እንዲከታተሉ፣ የንሥር ተመልካችነት(watch dog)  ኃላፊነትን እንዲወጡ ቢደረግ፤     
እንዴው በአጠቃላይ ግን የግንባታ ሂደታችንን እኛም ከአክሱም በፊት የምንገነባው፣ ቻይኖችም ከቻይና ግንብ በፊት የሚሠሩት ባንመስል መልካም ይመስለኛል፡፡ ቅንዥላቶቻችን በዐጸደ ነፍስ ሆነው ይገረሙብናል፤ ‹አሁን እነዚህ የኛ ልጆች ናቸው?› ይሉናልና፡፡

ዛሬ ወደ ቢሮ እየመጣሁ በሬዲዮ ስለ አጭበርባሪ ልመናዎች እየሰማ ነበር፡፡ ራሳቸውን በሽተኛ አስመስለው ስለሚለምኑ ሰዎች፡፡ እጃቸውን አጣምመው፣ ሰውነታቸው አቁስለው፣ ዓይናቸውን  የጠፋ አስመስለው፤ ጀርባቸውን አጉብጠው ስለሚለምኑ ሰዎች፡፡ በአንዳንድ ሰዎች ላይ የሚታየው የጉዳት ምልክት ምንም ዓይነት ጥርጣሬን የማያመጣ ነው፡፡ 
በሰማነው ነገር ላይ እየተወያየን ስንመጣ መርካቶ ‹ቁስል ተራ› የሚባል ቦታ አለኮ አለኝ አንድ ሰው፤ ‹‹ምን የሚደረግበት›› ብዬ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ቁስል የሚሠራበት›› አለኝ፡፡ ‹‹እዚያ ትሄድና ገንዘብ ከፍለህ የምትፈልገውን ዓይነት ቁስል ይሠሩልሃል›› አለኝ፡፡ አይ መርካቶ! አለ ጸጋዬ ገብረ መድኅን፡፤ እስኪ የበለጠ የምታውቁ አካፍሉን፡፡   


ሰሚ ካጡ የሶማሌ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡፡
አንድ ሰው የጠፋች የአካባቢው ግመል ፍለጋ ጫካ ይገባል፡፡ ከብዙ መከራ በኋላ ያቺን ግመል አግኝቶ ከተማ ገባና ግመሏን ለባለቤቱ ሳይመልስ ሐሳቡን ቀይሮ ራሱ ያልባትና ይጋልባት ጀመር፡፡ ግመሏን ከአውሬ ለማዳን ጫካ ገብቶ የነበረው ሰውዬ እርሱ ራሱ ግመሏን መውሰዱ ብዙዎችን አስገረማቸው፡፡ ትንሽ ቆየና ከዚያች ከአንዷ ግመል ወተት እያለበ በግመሏ ላይ ተቀምጦ እየዞረ ለአካባቢው ሰው ወተት መሸጥ ጀመረ፡፡ ነገር ግን የግመሏ ወተት በአንድ ጊዜ ሀብታም ሊያደርገው አልቻለምና ሌላ ነገር አሰበ፡፡ በወተቱ ውስጥ ውኃ እየጨመረ ቀላቅሎ መሸጥ፡፡ ‹‹ሰውም ምነው የሰውየው አመሉም ወተቱም ተቀየረሳ›› እያለ ዝም ብሎ ይገዛ ጀመር፡፡ (ይገዛ የሚለው ቃል ጠብቆ እንዳይነበብ አሳስባለሁ) 

ሰውዬውም በግመል ወተቱ ላይ ውኃን እያበዛው፤ የግመሉም ቁጥር እየጨመረ ሄደ፡፡ እየቆየም በግመልና በግመል ወተት ከሚታወቁት የሀገሩ ነጋዎች በላይ እኔ ነኝ ያለ፣ ቢጠሩት የማይሰማ ሀብታም ሆነ፡፡ የአካባቢው ሰዎችም ‹‹ይኼ ሰው ትናንት ምንም አልነበረውም፡፡ የጠፋ ግመል ሊፈልግ ጫካ ገባ፤ ተመልሶ መጣ፤ ከተማ ገባ፤ በአንድ ጊዜ ተመነደገ›› እያሉ ይገረሙ ነበር፡፡ ወተት ብቻ ተሽጦ እንዴት በሁለት ዓመት ሦስት መቶ ግመል ሊገዛ ቻለ፡፡ የሚለው የሕዝቡ ሁሉ ወሬ ሆነ፡፡ 
 
ሰውዬው ግን ምንም አልመሰለው፤ በወተቱ ውስጥ ውኃውን እየጨመረ ቀጠለ፤ እንዲያውም እበላ ባይ ቱልቱላዎችን ቀጠረና የእርሱ ወተት ሰው ጠጥቶት የማያውቅ መሆኑን እንዲለፍፉ አደረ፡፡  አንዳንድ ጊዜ እንዲያውም ወተቱን ለመልኩ ብቻ ይጨምርበትና የቀረው ውኃ ያደርገው ነበር፡፡ ‹‹ኧረ ሕዝቡ እያማረረ ነው፤ በአንድ በኩል በድንገት ተነሥህ፤ ከተማ ገብተህ ቢጠሩህ የማትሰማ ሀብታም ሆንክ፤ ይኼንን ስንታገሥህ ደግሞ ወተቱን ቀንሰህ ውኃውን እያበዛህ መሸጥ ጀመርክ፡፡›› ሲሉት ‹‹ተውት ባካችሁ፣ ለመሆኑ የእኔን ወተት ከመግዛት ውጭ ሕዝቡ ምን አማራጭ አለው፤›› ይል ነበር፡፡
 
በወተቱ ውስጥ የሚጨመረው ውኃም እየበዛ፣ ግመሎቹም እየበዙ ሄዱ፡፡ ግመሎቹም ሀገሩን ሞሉት፡፡ የሚያድሩበትና የሚግጡበት ልዩ የከተማ መሬት ተሰጣቸው፡፡ ወንዝ ዳር የሚገኝ ለም መሬት፡፡    
 
አንድ ቀን ሸበሌ ወንዝ አጠገብ ግመሎቹን አሠማርቶ እርሱ አንድ ዛፍ ጥላ ሥር ሻሂ ከልጁ ጋር ይጠጣ ነበር፡፡ በዚህ መሐል ከደጋ የዘነበ ዝናብ ወንዙን ሞላውና በግራ በቀኝ ሲግጡ የነበሩትን ግመሎች ጠራርጎ ወሰዳቸው፡፡ የጎርፉን ድምጽ ሰምተው አባትና ልጅ ከጥሻው ሲወጡ ግመሎቻቸው ሁሉም ተወስደዋል፡፡ እሪታውን ሰምተው የተሰበሰቡ የሀገሩ ሰዎችም በአግራሞት የሆነውን ነገር ይመለከቱ ነበር፡፡ 
 
‹‹አየህ›› አሉት አንድ አዛውንት ‹‹ያ በወተቱ ላይ እየጨመርክ የሸጥከው ውኃ ተጠራቅሞ፣ ተጠራቅሞ ጎርፍ ሆኖ ግመሎቹን ወሰዳቸው፡፡ ግፍ እንደዚህ ነው፡፡ ሲሠራ ቀላል ይመስላል የተጠራቀመ ዕለት ግን ጎርፍ ሆኖ ይወስዳል፡፡ ተው ብንልህ አልሰማ ብለህ ነበር፤ አንተ በግፍ ግመል ስትሰበስብ የግፉ ውኃ ሌላ ቦታ እየተሰበሰበ መሆኑን ረስተህዋል፡፡ ቀን ጠብቆ ግን ይሄው ጎርፍ ሆኖ መጣ›› አሉት፡፡
 
ግፍና ጎርፍ፡፡

በዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም ተነሥቶ የነበረው እሳት በደቅ ደሴት ሕዝብ፣ በገዳማውያኑና በፖሊስ ትብብር መጥፋቱ ተነገረ፡፡ እሳቱ ቁጥቋጦዎችን ከማጥፋት በቀር ደኑን እንዳላወደመው ተነግሯል፡፤ የደቅ ደሴት ሕዝብ ላደረገው አስቸኳይ ርብርብ ገዳማውያኑ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የክልሉ መንግሥትም ሄሊኮፕተር ለመላክ እስከመዘጋጀት ድረስ ያሳየውን ትብብር ገዳማውያኑና ሕዝቡ አድንቀዋል፡፡


እሳቱ ከደኑ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ እንዳያልፍ መነኮሳቱ፣ ፖሊስና ሕዝቡ ቆርጠውታል፡፤ በአፈር ከተር በመሥራት የእሳቱን ተሻጋሪነት ቀንሰውታል፡፡ አሁን እሳቱን ለማጥፋት እየተረባረቡ ነው፡፡

በጣና ሐይቅ ውስጥ በሚገኘው የዳጋ እስጢፋኖስ እሳት መነሣቱን የገዳሙ ምንጮች ተናግረዋል፡፤ እሳቱ የተነሣው ከደኑ አካባቢ ሲሆን ወደ ገዳሙ ገና አልደረሰም፡፡ የክልሉ ፖሊስ ወደ ቦታው በፍጥነት መድረሱ ተሰምቷል፡፡ አባቶች እሳቱን ቆርጦ ለመከላከል እየሞከሩ ነው፡፡ በሰው ኃይል ለመከላከል የማይቻል ከሆነ አስፈላጊውን ሁሉ እንደሚያደርግ ክልሉ ገልጦላቸዋል፡፡


ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በሚነሡ መድረኮች ላይ አንድነትና ኅብር ዋና መከራከሪያዎች ናቸው፡፡ አንዳንዶቻችን የብሔረሰቦች ተናጥላዊ መብትና ማንነት እየጎላ መምጣት፣ ሰዎችም ለአካባቢያዊ ማንነታቸው፣ ቋንቋቸውና ባሕላቸው ይበልጥ እያሳሱ መሄድ ኢትዮጵያዊ የሚባለውን ማንነት እንዳያጠፋውና ቆይቶም ኢትዮጵያ የምትባለውን አንዲት ሀገር እንዳይበታትናት እንሰጋለን፡፡ ሌሎቻችን ደግሞ ኢትዮጵያዊ የሚባለው ባሕል፣ ማንነት፣ ታሪክና ግዛት በውስጡ የሚገኙትን ልዩ ልዩ ቋንቋ፣ ባሕል፣ ታሪክ፣ ማንነት፣ያላቸውን ብሔረሰቦች እንዳይውጣቸው፣ ህልውና እንዳይነፍጋቸው፣ መብታቸውን እንዳይነፍጋቸው እንፈራለን፡፡
በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ አንድነትንና ልዩነቶችን(ኅብርን) አስታርቆና አስማምቶ እንደመጓዝ ያለ ፈታኝ የቤት ሥራ የለም፡፡ ሁለቱም የሀገሪቱ እውነታዎች ናቸውና፡፡ ኢትዮጵያ የምትባል ሁላችንንም እንደሰበዝ ያያያዘችና የያዘች ሀገር አለችን፡፡ ከነ ልዩ ታሪኳ፣ ማንነቷ፣ ባሕሏና ስሜቷ፡፡ ደግሞም እያንዳንዳችን ቀየ፣ ጎጥ፣ ጎሳ፣ ነገድ፣ ብሔረሰብ አለን፡፡ ከነ ልዩ ታሪኩ፣ ባሕሉ፣ ቋንቋው፣ ልማዱና ወጉ፡፡
ጥያቄው እንዴት ሳይጣሉና ሳይጠፋፉ እናስኪዳቸው ነው፡፡

እንደ እኔ እንደ እኔ ኢትዮጵያዊ የምንለው የሁላችንም የሆነው፣ ማንነት፣ ታሪክ፣ ባሕል፣ ሀገር፣ ዜግነትና ክብር ብሔረሰባዊ ማንነትን፣ ታሪክንና ባሕልን ሳይድጠው፣ ሳይውጠው፣ ሳያጠፋውና ሳይመጠው፣ ሳይጨፈልቀውና ሳይጠቀልለው፤ የብሔረሰብ ማንነት፣ ታሪክ፣ ባሕልና ልማድም ኢትዮጵያዊ አንድነትን ሳይከፋፍለውና ሳይበታትነው፤ ሁለቱም ያለ መነጣጠልና ያለ መጠፋፋት፣ በተዐቅቦ ተዋሕደው፤ አካባቢያዊ ባሕል፣ ቋንቋ፣ ልማድና ማንነት ለኢትዮጵያዊነት ውበቱ፣ ጌጡ፣ ሀብቱ፣ ሰበዙና አክርማው ሆኖ፤ ኢትዮጵያዊነትም ለአካባቢያዊ ማንነት ኩራቱ፣ የጋራ መገለጫው፣ መዋሐጃውና መግባቢያው፣ በጋራም የሚገነባው የተግባቦት ቤቱ ሆኖ፤ የአንዱ መኖር ሌላውን ሳያጠፋው፤ የአንዱ መኖርም ሌላኛውን ሳያስክደው፤ አካባቢያዊ ማንነት ለኢትዮጵያዊነት መጋቢው ጅረቱ፣ ኢትዮጵያዊነትም ለየአካባቢያዊ ማንነት መሰባሰቢያው፣ መታያው፣ ዓባዩ ሆኖ፤ አካባቢያዊነት ግብዐቱ፤ ኢትዮጵያዊነት ወጡ፤ አካባቢያዊነት ድርና ማገሩ፣ ኢትዮጵያዊነትም ጋቢና ቀሚሱ፤ አካባቢያዊነት ፊደሉ፤ ኢትዮጵያዊነት ጽሕፈቱ፤ አካባቢያዊነት ቃሉ፣ ኢትዮጵያዊነት ድርሰቱ፣ አካባቢያዊነት ብሎኬት፣ ኢትዮጵያዊነት ሕንጻ፤ አካባቢያዊነት ብልት፣ ኢትዮጰያዊነት አካል ሆኖ መኖር ያለበት ይመስለኛል፡፡
ኢትዮጵያዊነት የሁላችን ድምር ውጤት፣ የሁላችንም የጋራ ቤት፣ የሁላችንም ማንነት ውሕደት ያስገኘው ልዩ የሆነ ማንነት ነውና ከአካባቢያዊ ማንነቶች ሁሉ ይሰፋል፣ ይበልጣልም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከአካባቢያዊ ማንነት የሰፋ ለየት ያለ ማንነት ያላቸው፤ እንዲያውም አካባቢያዊ ማንነትም የሌላቸው ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡ ከተለያዩ ጎሳዎች፣ ነገዶችና ማንነቶች ከመጡ ቤተሰቦች የተገኙ፤ አንድ ብቻ የሆነ ማንነት የሌላቸው፤ ሦስትና አራት ማንነቶችን ያዋሐዱ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡ እነዚህን የዚህ ጎሳ፣ ነገድ፣ አካባቢ ሰዎች ማለት አንችልም፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሌላ ሀገር ተወልደው፣ ኢትዮጵያዊ ዜግነትን አግኝተው፣ ነገር ግን ከኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ከአንዱ ያልተወለዱ ኢትዮጵያውያንም አሉ፡፡ እነዚህን ሁሉ የሚጠቀልል ነው ኢትዮጵያዊነት፡፡  
ኢትዮጵያዊና አካባቢያዊ ማንነት ተጣጥሞ የመሄጃው መንገድ የተዐቅቦ ተዋሕዶ ይመስለኛል፡፡ ተዐቅቦ ማለት ሁለቱም በየራሳቸው ራሳቸውን እያሳደጉ፣ አንዱ አንዱን ለማጥፋት፣ ለመደፍጠጥና ለመጨፍለቅ፣ ለመበታተንና ለመሰነጣጠቅ ሳይሠራ፣ ሂደቱን ለተፈጥሯዊ ሂደት ትቶ ነገር ግን ዕውቅና ተሰጣጥቶ መኖር ማለት ነው፡፡ ተዋሕዶ ስንል ደግሞ አካባቢያዊ ማንነት ኢትዮጵያዊነትን ገንዘቡ አድርጎ፤ ኢትዮጵያዊ ማንነትም አካባቢያዊ ማንነትን ገንዘቡ አድርጎ፤ በተቃርኖ ሳይሆን በተዋሕዶ መኖር ነው፡፡ በተዐቅቦ ምክንያት መለያየት እንዳይመጣ ተዋሕዶ እያረቀው፤ ተዋሕዶ  መጠፋፋትን እንዳያስከትል ተዐቅቦ እያቀናው፡፡ ኢትዮጵያዊነት ሲባል የአካባቢያዊ ማንነቶች ድምር ውጤት ብቻ ሳይሆን በሂደት ተጣጥመውና ተገናዝበው የፈጠሩት የላቀ አንድ ውሑድ ማንነት ሆኖ መጓዝ ነው፡፡ 
ይህንን ሂደት ውጤታማ ለማድረግ ሦስት ነገሮች የሚያስፈልጉ ይመስለኛል፡፡ ማከም፣ መተዋወቅና ነጻነት፡፡ በታሪክ ሂደት ውስጥ ሕዝቦችን እንወክላለን የሚሉ አካላት ተጋጭተዋል፡፡ መቼም ሕዝብ ለሕዝብ መክሮና ወስኖ አይጋጭምና፡፡ እነዚህ ግጭቶች በአንደኛው ወይም በሁሉም ላይ ትተውት የሚያልፉት ቁስል አለ፡፡ ይህንን ቁስል እንዲያመረቅዝ በየጊዜው ኮምጣጤ ከመጨመር ይልቅ ወደ ማከም ብናደላ መልካም ነው፡፡ በነበሩት ችግሮች ላይ በይፋ ተወያይቶ፤ በችግሮቹ ላይ ተግባብቶ አብሮ መፍትሔውን መፈለግ፡፡ ትናንትን ምንም ልናደርገው አንችልም፡፡ አልፏል፡፡ ልናክመው ብቻ ነው የምንችለው፡፡ ነገን ግን እንደምንፈልገው አድርገን መቅረጽ እንችላለን፡፡ አሁን እንደሚታየው ቁስሉን እየገላለጥን ታማሚውን አካል ይበልጥ እንዲያመው አድርገን ከመተው ይልቅ፣ ቁስሉን ገላልጦ ትክክለኛውንም ሕክምና ሰጥቶ ማዳን ያስፈልገናል፡፡
በርግጥ ሕመም የህልውናቸው መሠረት የሆኑ አካላት አሉ፡፡ ልክ አንዳንድ ነዳያን ቁስላቸውን ለልመና እንደ ሚጠቀሙበት፤ ከቁስል መዳናቸውን ሳይሆን ራሱን ቁስሉን ለገበያ እንደሚፈልጉት ሁሉ የሕዝቦችን ቁስልም ለገበያ የሚፈልጉት አካላት ይኖራሉ፡፡ የሚያተርፉት ከቁስሉ በመሆኑ ምንጊዜም ስለቁስላችንና ማን እንዳቆሰለን እንጂ እንዴት ልንድን እንደምንችል አይነግሩንም፡፡ መድኃኒቱን አያሳዩን፡፡  ቁስለኞቹ ግን መዳኑን እንፈልገዋለን፡፡ ለዚህ ነው ማከም አለብን የምለው፡፡ አንድ በሽተኛ የሕመሙን ዓይነትና ምክንያት ማወቁ ብቻ ለድኅነት አያበቃውም፡፡ እንዴት ሊድን እንደሚችል ማወቅ፣ መድኃኒቱንም ማግኘት ይበልጥ ይጠቅመዋል፡፡ በኢቦላ በሽታ ያለቁ የምዕራብ አፍሪካ ወገኖቻችን፣ የበሽታውን መነሻና አስተላላፊ ዐውቀውታል፡፡ የቸገራቸው መድኃኒቱ ነው፡፡
ሁለተኛው ደግሞ መተዋወቅ ነው፡፡ አጥር ከመሥራት ድልድይ መሥራት፤ ድንበርተኛ ከመሆን በረኛ መሆን የተሻለ ሕይወት ይሰጠናል፡፡ ሁሉም በአካባቢው ቋንቋ መማሩና ቋንቋውን ማደሳደጉ መልካም ነው፤ መብትም ነው፡፡ ቋንቋ ግን በራሱ ሰዎች ብቻ አድጎ አያውቅም፡፤ እንግሊዝኛ ያደገው በእንግሊዞች ብቻ አይደለም፡፡ ከጃፓን እስከ አሜሪካ ያሉት ሁሉ ተሳትፈውበት ነው፡፡ ተምረውት፤ ዐውቀውት፤ ተጠቅመውበት ነው፡፡ አማርኛን ያሳደጉት ‹አማሮች› ብቻ አይደሉም፡፡ እንዲያውም ከጥንት ጀምሮ የአማርኛን ሥነ ጽሑፍ ያሳደጉት ‹አማራ› ከሚባለው የተለምዶ አካባቢ ውጭ ያሉ ሊቃውንት ናቸው፡፡ አማርኛ የኢትዮጵያ ጎሳዎች፣ ነገዶችና ወገኖች ሁሉ ተሳትፈውበት ነው ያደገው፡፡
ዛሬም የሌሎችን ወገኖቻችንን ቋንቋዎች እናሳድግ ካልን መፍትሔው አጥር ሠርቶ ለብቻ መነጋገር ሳይሆን ሌሎችም እንዲያውቁት፣ እንዲጠቀሙበትና ገንዘብ እንዲያደርጉት ማብቃት ነው፡፡ አሁን የምንከተለው የአንድ ቋንቋ ፖሊሲ የሚያዋጣ አይመስለኝም፡፡ አንድ ሰው ኦሮምኛን ለመቻል ኦሮሞ፣ ሶማልኛን ለመቻል ሶማሌ፣ ትግርኛን ለመቻል ትግራዊ የመሆን ግዴታ ሊኖርበት አይገባም፡፡ ከዚህ ይልቅ በአንድ አካባቢ ያሉ ኢትዮጵያውያን ከክልላቸው ቋንቋ በተጨማሪ ሌሎች ቋንቋዎችን የሚያውቁበት መንገድ መፈጠር አለበት፡፡ ቢያንስ ሶማልኛ፣ ትግርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ሲዳምኛ፣ ወላይትኛ በሁሉም ክልሎች በአማራጭነት ቀርበው፤ አንድ ተማሪ ከክልሉ ቋንቋና ከፌዴራሉ ቋንቋ በተጨማሪ ቢያንስ ሁለቱን ጨምሮ እንዲማር መደረግ አለበት፡፡ ቋንቋ መለያያችን ሳይሆን መግባቢያችን መሆን እንዲችል፡፡ ቋንቋ አጥር ሳይሆን ድልድይ እንዲሆን፡፡
ዛሬ ዛሬ በአንዳንድ ክልሎች ከሌሎች ክልሎች ከሚመጡ ወገኖቻችን ይልቅ የውጭ ሀገር ሰዎች የተሻለ ነጻነት ይሰማቸዋል፡፡ ከክልላቸው ውጭ የሥራ ዕድል ለማግኘት(መያድ ካልሆነ በቀር) የማይችሉ የአንዳንድ ክልሎች ሰዎች አሉ፡፡ ይኼ ሁኔታ በሕዝቦች መካከል መጠራጠርን፣ አለመግባባትንና በጠላትነት መተያየትን ይፈጥራል፡፡ እየቆየ ደግሞ ቂምና በቀልን ለትውልድ ያኖራል፡፡ እያንዳንዱ በሌላው ክልል የደረሰበትን በራሱ ክልል ሲበቀል አገሪቱ የማያልቅ አዙሪት ውስጥ ትገባለች፡፡ የወደፊቱን እያሰበች ከመጓዝ ይልቅ ትናንት የተፈጠሩትንና ዛሬ የሚያገረሹትን ችግሮች በመፍታት ላይ ትጠመዳለች፡፡ ለዚህ ነው ኢትዮጵያውያን በየትኛውም ክልል ተዘዋውረው ሲኖሩና ሲሠሩ ነጻነት እንዲሸታቸው፤ ደኅንነት እንዲሰማቸው ማድረግ የሚያስፈልገው፡፡ ኢትዮጵያውያን ነጻነትና ደኅንነት የሚሰማቸው በክልላቸው ውስጥ ብቻ ከሆነ ዐውቀንም ይሁን ሳናውቅ በአንዲት ሀገር ውስጥ ሊግባቡ የማይችሉ ብዙ ሀገሮች እየፈጠርን ነው ማለት ነው፡፡   
ለዚህ ነው የተዐቅቦ ተዋሕዶ ይሻለናል ያልኩት፡፡ መጠፋፋትን በተዐቅቦ፣ መለያየትን በተዋሕዶ፤ ማጠቃለል ዝርዝሮችን ያስረሳል፤ መዘርዘር ደግሞ ጠቅላላን ነገር ያጠፋል፡፡ ዝርዝርን በተዋሕዶ፤ ጥቅለላን በተዐቅቦ፤ የከረረ አካባቢያዊነት ብሔራዊነትን ይንዳል፤ የተለጠጠ ብሔራዊነትም አካባቢያዊነትን ይጨፈልቃል፣ ስለዚህም ብሔራዊነትን በተዐቅቦ፣ አካባቢያዊነትን በተዋሕዶ እያረቅን ኢትዮጵያን ወደ ልዕልና እንውሰዳት፡፡ መገናዘብ(አንዱ ሌላውን ገንዘቡ ማድረግ) እንጂ መጠፋፋት ለዚህ አይበጀንም፡፡

 

(በብዙ አንባቢያን ጥያቄ በድጋሚ የታተመ)

 
የገና እና የጥምቀት በዓላት ሲደርሱ በምእመናኑ ዘወትር የሚጠየቁ ጥያቄዎች አሉ፡፡ እነዚህን እና መሰል የሕዝቡን የዘወትር ጥያቄዎች መልስ የያዘ የማያዳግም ጥራዝ ማውጣት ከሊቃውንት ጉባኤ የሚጠበቅ ነው፡፡ አብዛኞቹ ጉዳዮች አበው ቀድመው ሥርዓት የሠሩባቸው እና ማብራርያ ብቻ የሚያስፈልጋቸው ናቸውና፡፡ ለዛሬ ሦስቱን ብቻ እንመልስ፡፡
 
ገና እና ጥምቀት ዓርብ እና ረቡዕ ቢውሉ ይበላባቸዋል ወይስ ይጾማሉ?
ፍትሐ ነገሥት፡ ዳግመኛ በየሳምንቱ ዓርብ እና ረቡዕን መጾም ነው፡፡ በዓለ ሃምሳ፣ የልደት እና የጥምቀት በዓል የተባበሩባቸው ጊዜ ካልሆነ በቀር /ዐንቀጽ 15፣ ቁ566/

የዓርብን እና የረቡዕን ጾም ግን ከልደት፣ከጥምቀት እና ከበዓለ ሃምሳ በቀር ዘወትር ይጹሙ /ዐንቀጽ 15፣ቁ 603/
የገና እና የጥምቀት ቅዳሴ ስንት ሰዓት ነው?
ፍትሐ ነገሥት፡ ስለ ልደት እና ጥምቀት ግን በዚያ ዘመን በኒቂያ የተሰበሰቡ ሊቃውንት ቅዳሴው በሌሊት ይሆን ዘንድ አዘዙ /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 595/
ልደት ጋድ አለው?
ፍትሐ ነገሥት፡ የልደት እና የጥምቀት በዓላት ጋድ አላቸው /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 566/
     ትንታኔ፡ የገና ጾም 44 ቀናትን ይይዛል፡፡
                   40 ጾመ ነቢያት
                     3 ጾመ አብርሃም ሶርያዊ
                    1 ጋድ
               ድምር 44
የገና ጋድ ከጾሙ ተያይዞ የተቀመጠ እንጂ ለብቻው የተቀመጠ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ሰሙነ ሕማማት ለብቻው የሚቆጠር ጾም ነው፡፡ /ዐንቀጽ 15፣ቁ 565/ ነገር ግን አንድ ሰው ዐቢይ ጾምን ሳይጾም ከርሞ ሕማማትን ለብቻው መጾም አይችልም፡፡ የገናም ጋድ እንዲሁ ነው፡፡
ይህንን ጋድ የልደትን ጾም የማይጾሙ ሰዎች እንዲጾሙት የተሠራ ነውን?
መልስ፡ በቤተ ክርስቲያን ላልተጠመቁ፣ ለማይቆርቡ፣ ንስሐ ለማይገቡ፣ ለማያስቀድሱ፣ ለማይጾሙ ሰዎች ተብሎ የተሠራ ልዩ ሥርዓት የለም፡፡ በፍትሐ ነገሥት ዐንቀጽ 15፣ ቁ 565 እንደተገለጠው ሰባቱ አጽዋማት «ለክርስቲያን ሁሉ» የታዘዙ ናቸው፡፡ ስለዚህም የገናን ጾም ክርስቲያን ሁሉ ጾመው በበዓለ ልደት ሊገድፉ ይገባቸዋል፡፡ ፍትሐ ነገሥት ስለ ገና ጾም ሲገልጥ «መጀመርያው የኅዳር እኩሌታ ፋሲካው የልደት በዓል ነው» ይላል /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 568/፡፡ ይህም ከገና ጾም ተሸርፎ የሚጾም ነገር እንደሌለው ያሳያል፡፡
መልካም በዓል

The Indian Folktales በተሰኝ ከዛሬ 100 ዓመት በፊት በ1919 እኤአ በታተመ መጽሐፍ ላይ እንዲህ ይላል፡፡
አንድ የሕንድ ጠቢብ ደቀ መዝሙሮቹን ሥራ እንዲሠሩ አዘዛቸውና ራቅ ብለው በከፍታ ቦታ ላይ ይመለከታቸው ጀመር፡፡ ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ተመልሶ ደቀ መዝሙሮቹን ሰበሰባቸው፡፡ ከዚያም እንዲህ አላቸው ‹‹ከእናንተ መካከል የተወሰናችሁ እንደ ሰው የተወሰናችሁት ደግሞ እንደ እንስሳ ስትሠሩ ነበር›› ተማሪዎቹም ተገርመው ጠየቁት፡፡ መምህሩም ‹‹እንደ እንስሳ መሥራት ማለት አንድን ነገር መጎተት፣ መሸከም፣ መግፋት፣ ማዞር ወይም የሚደርስበት ቦታ ማድረስ ማለት ነው፡፡ ምን እየሠራ እንደሆነ፣ ለምን እየሠራ እንደሆነ፣ የሚመጣው ውጤት ምን እንደሆነ፣ ዓላማው ምን እንደሆነ አያስብም፡፡ በሥራው ላይም ከራሱ አስቦ አንዳች አይጨምርም፡፡ የዛሬ ሺ ዓመት አንድ ዝሆን የሠራውን ዛሬም ሌላ ዝሆን በተመሳሳይ መልኩ ይሠራዋል፡፡(አንድ ሊቅ ‹ዕብደት ማለት አንድ ውጤት እንደማያመጣ እየታወቀ በተደጋጋሚ መሥራት ነው› ብሎ ነበር) አያሻሽለውም፡፡ ምናልባት ከሰው በላይ ተሸክሞ፣ ስቦ፣ ገፍቶ፣ ቆፍሮ፣ ሮጦ፣ ደክሞ፣ ይሆናል፡፡ ያ ግን እንስሳውን ጠንካራ ያስብለዋል እንጂ ጎበዝ አያስብለውም፡፡ጉብዝና አእምሮ አለበት፡፡ እንደ እንደስሳ የሚሠሩ ሰዎች እንጂ እንደ ሰዎች የሚሠሩ እንስሳት የሉም የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ 

እንደ እንስሳ የሚሠሩ ሰዎች እንደዚህ ናቸው፡፡ የተሰጣቸው ሥራ ያለ መለገም ይሠራሉ፡፡ ሲቆፍሩ፣ ሲገነቡ፣ ሲያመላልሱ፣ ሲያርሱ፣ ሲያጭዱ፣ ሲሸከሙ፣ ሲሰፉ፣ ሲፈጩ ይውላሉ፡፡ የሚሠሩት ያለ የሌለ ጉልበታቸውን ሁሉ ተጠቅመው ነው፡፡ ነገር ግን ጉልበታቸው እንጂ አእምሯቸውን አያሠሩትም፡፡ አርባ ዓመት፣ ሃምሳ ዓመት ተመሳሳይ የሆነን ሥራ ያለ ምንም ማሻሻል ሲያከናውኑ ታያላችሁ፡፡ የጻፉት ወረቀት፣ የሰፉት ልብስ፣ ያመረቱት እህል፣ የሠሩት ቤት ምን እንደሚሆን አያስቡም፡፡ እስኪ ቀየር አድርገን፣ አሻሽለን፣ ለውጠን፣ በተለየ መንድ እንሥራው አይሉም፡፡ ስለዓላማው፣ ስለሚከተለው ነገር፣ ስለሚያደርጉት ጥንቃቄ፣ ስለ ዕውቀት መሻሻል ምንም ነገር አያስቡም፡፡ እንዲያውም አእምሮ ያለው መጥቶ ለውጥ ሲያመጣባቸው ዓለም ያለፈች ይመስላቸዋል፡፡ ታላቅነታቸውን የሚያስመሰክሩት ያንን ብቻ በማድረግና ያን ጠብቆ በመኖር ነው፡፡ ለምን እንደሚያደርጉትና ለምን እንደሚጠብቁት ግን አያውቁም፡፡ብቻ ያ ነው ሥራቸው፡›› አላቸው፡፡
ተማሪዎቹም ራሳቸውን ነቀነቁ፡፡ ‹‹ከእናንተ መካከል አንዳንዶቻችሁ እንደ ሰው አንዳንዶቻችሁም እንደ እንስሳ ስትሠሩ አየኋችሁ፡፡›› አለ መምህሩ፡፡ ተማሪዎቹም ‹‹እንደ ሰው መሥራት ምንድን ነው? መለኪያውስ ምንድን ነው?›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ መምህሩም እንዲህ አላቸው፡፡ ‹‹እንደ ሰው መሥራት ማለት ቢያንስ እነዚህን አራት ነገሮች ለማድረግ መቻል ነው፡፡
1.       ሥራን ሲሠሩ የሚያስከትለው ውጤት ዐውቆ መሥራት፡- ሥራን ስትሠሩ ምን ውጤት ያመጣል? ዓላማው ምንድን ነው? የእኔ ድርሻ ምንድን ነው? የሚያስከትለው በጎና ክፉ ነገር ምን አለ? የዚህ ሥራ ትልቁ ሥዕል ምንድን ነው? ብላችሁ አስቡ፡፡ ድንጋይ ፍለጡ ስለተባላችሁ፣ ጉድጓድ ቆፍሩ ስለተባላችሁ ወይም ልብስ ሥሩ ስለተባላችሁ በቻ አትሥሩ፡፡ እናንተ የምትሠሩት ሥራ የመጨረሻው ውጤቱ ምን እንደሆነ አስባችሁ ሥሩ፡፡ ያ ከሆነ ለጥራት ትጨነቃላችሁ፤ለውበት ታስባላችሁ፤ ሀገራችሁን፣ ሕዝባችሁን እያሰባችሁ ትሠራላችሁ፡፡ ራሳችሁን የታላቅ ዓላማ አካል እንጂ የአንዲት ቁራጭ ሥራ ሠራተኛ አታደርጉትም፡፡
2.     በጥንቃቄ መሥራት፡– ማንኛውም ሥራ የሚያመጣው በጎና ክፉ ነገር ይኖራል፡፡ ሰው ማለት ክፉን ነገር እየቀነሰ በጎን ነገር እያበዛ የሚሄድ ፍጡር ነው፡፡ የምትሠሩት ሥራ ጥፋት እንዳያስከትል፣ ጉዳት እንዳያመጣ፣ ሌሎችን እንዳይረብሽ፣ ሌሎች የሠሩትን እንዳያበላሽ፣ አስባችሁ ሥሩ፡፡ የእናንተን ሥራ መሥራትና የተሰጣችሁን መጨረሳችሁን ብቻ የምታዩ ከሆነ ሰዎች ሳትሆኑ እንስሳት ሆናችኋል ማለት ነው፡፡ እያሰባችሁ አይደለም ማለት ነው፤ ጡንቻችሁ እንጂ አእምሯችሁ አላደገም ማለት ነው፡፡ ለተሰጣችሁ ዕቃ፣ ለሰውነታችሁ፣ ለጤናችሁ፣ ለአካባቢያችሁ፣ ለሌሎች ሰዎች፣ ለእንስሳት፣ ለዕጽዋት፣ ጥንቃቄ አድርጉ፡፡ ስትሠሩ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳታስከትሉ ተጠንቀቁ፤ ጉዳት ቢመጣ እንኳን ለመቀነስ ጣሩ፡፡ ግዴለሾ አትሁኑ፡፡ ግዴለሽ ሰው ሠራተኛ አይባልም፤ አጥፊ እንጂ፡፡
3.     ከሚጠበቀው በተሻለ መሥራት፡ የተሰጣችሁን ሥራ ከተሰጣችሁ በተሻለ መልኩ በመሥራት ከሚጠበቅባችሁ የበለጠ ውጤት አስመዝግቡ፡፡ ያንኑ የተሰጣችሁን ብቻ የምትሠሩ ከሆነማ ከእንስሳ ምኑን ተሻላችሁት፡፡ አንድን ዝሆን ዕቃ አሸክመን ብንልከው፤ በዝሆን ፍጥነት ተጉዞ ዕቃውን ያደርሳል እንጂ ፍጥነቱን ስለማሻሻልና በአቋራጭ መንገድ ስለ መጠቀም አያስብም፡፡ እናንተም እንዲሁ የተሰጣችሁን ብቻ የምትሠሩ ከሆነ ጠንካራ ልትሆኑ እንጂ ጎበዝ ልትሆኑ አትችሉም፡፡ ጎበዝ ማለት ስለ ተሻለ ነገር ለማሰብ የሚችል ማለት ነው፡፡
4.     በዕውቀት ላይ ተመሥርቶ መሥራት፡- ሥራን ስትሠሩ ዐውቃችሁት ሥሩ፤ መለካት ካለባችሁ በመለኪያ ተጠቀሙ፤ መመዘን ካለባችሁ በመመዘኛ ተጠቀሙ፤ እናውቀዋለን፣ ለምደነዋል ብላችሁ በግምት አትሥሩ፡፡ የተሰጣችሁ መመሪያ ካለ እርሱን ተከተሉ፤ የተሰጣችሁን ዝርዝር ሥራ ተመልከቱና የጎደለ ወይም የማያስፈልግ ካለ አስተክክሉ፤ መቼ ጀምራችሁ መቼ መጨረስ እንዳለባችሁ አስቡ፡፡ ምንም የተማራችሁና ዐዋቂዎች ብትሆኑ ስለምትሠሩት ሥራ መጀመሪያ ጠይቁና ተረዱ፤ አስፈላጊ መሣሪያ ሳትይዙ አትሥሩ፡፡ እናውቀዋለን ከምትሉ ላናውቀው እንችላለን ብላችሁ ለማወቅ ሞክሩ፡፡
እንስሳ ዕውቀት የለውም፤ የሚሠራውን በዕውቀት ተመርቶ አይሠራም፡፡ ስለ ጫኑት ይጫናል፤ ስለ ጎተቱት ይሄዳል፤ ስላረሱበት ያርሳል፡፡ እናንተ ግን ጉልበታችሁን አእምሯችሁ ይምራው፡፡ ይህ ነው እንደ ሰው መሥራት ማለት፡፡››
እኛስ እንዴት እየሠራን ነው? እንደ ሰው ወይስ እንደ እንስሳ?

ጥር
በልዩ ቅናሽ የመጻሕፍት ሽያጭ ወር
አግዮስ ኅትመትና ጠቅላላ ንግድ ሥራ ሐላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ያሳተማቸውን
የዲያቆን ዳንኤል ክብረትና የሌሎችንም መጻሕፍት፤ የንባብ ባህላችንን ለማሳደግ እና አንባብያንን ለማበረታታት፤ ከ25% እስከ 50% (ከሃያ አምስት እስከ ሃምሣ በመቶ) ቅናሽ በማድረግ፤
ከጥር 1 እስከ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ባሉት ቀናት ውስጥ ለአንድ ወር
የሚቆይ ልዩ የመጻሕፍት ቅናሽ ሽያጭ መርሐ ግብር አዘጋጅቷል፡፡
ቦታ፡- አግዮስ መጻሕፍት መደብር
አድራሻ፡- መገናኛ ለም ሆቴል አጠገብ፣ ማትያስ ሕንፃ ምድር ቤት (G – 06)
             ስልክ ቁጥር፡- 011 663 9902 / 0930098254
በተለይ ‹አራቱ ኃያላንን ላልገዛችሁ ይኼ መልካም አጋጣሚ ነው

ውድ አንባብያን መጻሕፍቱን በአዲስ አበባ ሌሎችም አካባቢዎች በወኪሎቻችን አማካኝነት በአቅራቢያቸው እንዲያገኙ፤
      ለጉርድ ሾላ፣ ሲ ኤም ሲ ሚካኤል እና አካባቢው፤
መዝገቡ መጻሕፍት መደብር፤ ጉርድ ሾላ ቴሌ ፊት ለፊት፣ ዲ ኤም መንጃ ፈቃድ ት/ቤት ሕንፃ ሥር፤
                               ስልክ ቁጥር፡- 0912 951732
      አራት ኪሎ / ቅድስት ማርያም / አካባቢ፤
ፍሬው መጻሕፍት መደብር፤ ዐፄ ናዖድ ት/ቤት አጠገብ ስልክ ቁጥር፡- 0911 685232

      ፒያሳ አራዳ ጊዮርጊስ አካባቢ፤
ጌታቸው መጻሕፍት መደብር፤ አራዳ ጊዮርጊስ ጤና ጣቢያ ፊት ለፊት፤ ስልክ ቁጥር፡- 0911 469954
መኮንን መጻሕፍት መደብር፤ ስልክ ቁጥር፡- 0913 108312


ታኅሣሥ 19 ቀን 2007 ዓም በቤተ ክርስቲያን ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ ከታወቁት ሊቃውንት መካከል አንዱን አጥተናል፡፡ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየን፡፡ ስለ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በመቆርቆር፣ በማስተማርና በመጻፍ የምናውቃቸው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱን ከጫፍ እስከ ጫፍ ያገለገሉ፤ በተለይም ለወጣቱ ትውልድ ጥያቄዎቹን በመመለስና አስረግጠውም በማስረዳት የምናደንቃቸው ነበሩ፡፡
ዜማ፣ አቋቋም፣ የአማርኛ ሰዋስው፣ ቅኔና የግእዝ አገባብ፣ ብሉይ፣ ሐዲስ፣ ነገረ መለኮት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ በዘመናዊ ትምህርት እስከ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የተማሩ መሆናቸውን ስናይ፤ በአንባቢነታቸው ጥንታውያንና ዘመናውያን መጻሕፍትን የሚያገላብጡ ብቻ ሳይሆኑ በላዔ መጻሕፍት እንደነበሩ በሌሎቹ ሊቃውንት ሲመሰከርላቸው፤ በምሥራች ድምጽ ሬዲዮ ትምህርት በመስጠት፣ በታሪክና ድርሰት ክፍል ለዐሥር ዓመታት በማገልገል፤ የመዝሙር ክፍልን በመምራት፣ የዜና ቤተ ክርስቲያንን በምክትልና በዋና አዘጋጅነት  በማገልገል፣ እንዲያውም ጋዜጣውን የጋዜጣ መልክ በማስያዛቸው በ1962 ዓም መሸለማቸውን  እያዘከርን የተጓዙበትን የዕውቀት ጎዳና ስንመረምር ያጣነው አንድ ሰው ብቻ ባለመሆኑ፡-
አራት ሰው ሞተ ተቀበረ ዛሬ
ድጓ ጾመ ድጓ መዋሥዕት ዝማሬ
ተብሎ ለሊቁ የተገጠመው ሙሾ ለእርሳቸውም ይስማማቸዋል እንላለን፡፡ 

የየረርና ከረዩ አውራጃ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ዋና ጸሐፊ፣ የቀበና አቦ አስተዳዳሪ፣ የካህናት አስተዳደር መምሪያ ጸሐፊ፣ የኤርትራ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የከፋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የትምህርትና ማሠልጠኛ መምሪያ ኃላፊ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የአስተዳደር መምሪያ ኃላፊ፣ የቁጥጥር አገልግሎት ኃላፊ፣ የበጀትና ንብረት መምሪያ ኃላፊ፣ የስብከተ ወንጌል መምሪያ ኃላፊ፣ የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህት ቤት ምክትል ዲን፣ እየሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱን ማገልገላቸው ስንመለከት፡-
ቀባሪዎቹን
አፈር መልሱ እንጂ ድንጋይ ለምናችሁ
የቀለም ቀንድ ነው ትሰብሩታላችሁ
እንላቸዋለን፡፡
በ1977 በምዕራብ ጀርመን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ዜማ ለማሳየት ከተጓዘው ልዑክ አንዱ ነበሩ፤ በ1995 የዓለም አብያተ ክርስቲያናት በእስክንድርያ ከተማ ባደረገው ጉባኤ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው ነበር፣ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ በአዲስ መልክ ሲዘጋጅ በብርቱ ካገለገሉት ሊቃውንት አንዱ ነበሩ፣ የመንና ጅቡቲ የሚገኙ ምእመናንን ለማስተማር በየዓመቱ ይጓዙ ነበረ፡፡ የሊቃውንት ጉባኤ አባል ሆነው ለብዙ ዓመታት አገልግለዋል፡፡ ይህንን ስንመለከትም
እንግዲህ መቃብር ጠንክረህ ተማር
ዕውቀት ተሸክሞ መጣልህ መምር
እንለዋለን፡፡
ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየ ሰንበት ትምህርት ቤቶች በሚያዘጋጁት ጉባኤ ልጆችን ሳይንቁ፣ ክፍለ ሀገር በሚዘጋጅ ጉባኤ ለመንገዱ ሳይሰቀቁ በመጓዝ ያስተማሩ የዘመናችን ሐዋርያ ናቸው፡፡ ክህነትን፣ ትምህርትንና ጽሕፈትን አንድ አድርገው የያዙ፤ በተለይም ‹‹ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን›› እንደ አንድ የትምህርት ዘርፍ ሆኖ እንዲወጣ በብርቱ የደከሙ ሊቅ ናቸው፡፡ ድካማቸው ፍሬ አግኝቶ በየጊዜው ያዘጋጇቸው መጣጥፎችና መጻሕፍት ዛሬ ከኮሌጆች እስከ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ድረስ የማስተማርያ ዋና መሣሪያዎች ሆነዋል፡፤ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንድ የትምህርት ዘርፍ ሆኖ እየተሰጠ ይገኛል፡፡
ሚያዝያ 19 ቀን 1929 ዓም  ይፋት ውስጥ  ደብረ ምሥራቅ ሾተል አምባ በኣታ አጥቢያ ተወልደው፣ በ1941 ዓም ከብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ዲቁና፣ በ1959 ዓም ቅስና ተቀብለው፤ አራት ወንዶችና አራት ሴቶች ወልደው፣ አሥር የልጅ ልጆች አይተው በ78 ዓመታቸው የተለዩን ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየ በዕለተ ዕረፍታቸውና ቀብራቸው ብዙዎችን ያስደነቁ ሁለት ነገሮች ተከስተዋል፡፡ የመጀመሪያው ክንፈ ገብርኤል ተብለው ተጠርተው በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ በዓል(ታኅሣሥ 19 ቀን) ወደ ፈጣሪያቸው መጠራታቸው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የቀብር ሥነ ሥርዓቱ ሲከናወን የሕይወት ታሪካቸው በሚነበብበት ጊዜ ከትልቅ ዋርካ ላይ ማንም ሳይነካው አንድ ትልቅ ቅርንጫፍ ተገንድሶ መውደቁ ነው፡፡
ቦታው የነበሩ፣ ይህንንም ነገር የተመለከቱ ሁሉ ታሪኩን በካሜራቸው ሲቀርጹና ከታላቋ ዋርካ ከቤተ ክርስቲያን ብዙዎችን የያዘው አንዱ ታላቅ ቅርንጫፍ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ዛሬ መሰናቱን በኀዘን ሲተረጉሙ ነበር፡፡ የቅርንጫፉን ቅጠልም ብዙዎቹ ተሻምተው ወስደውታል
በረከታቸው ይደርብን፡፡