በከፍተኛ የደህንነት ሃይሎች የሚመራ የእስር ዘመቻ በሙስሊሞች ላይ መከፈቱ ተገለፀ
ከ800 -1000 የሚደርሱ ሰዎችን በአዲስ አበባ ለማሰር ታቅዷል፡፡
የቢላል ሬዲዬ ጋዜጠኛ የነበረው ካሊድ ሙሃመድ በደህንነት ሀያሎች ታፍኖ ተወስዷል።
ህውሃት መራሹ ወያኔ አሁንም ንፁሃን ሙስሊሞችን ከየአካባቢው ማደነኑን ቀጥሏል። በዛሬው እለት በብርጭቆ አካባቢ ኮንዶሚኒየም ይኖር የነበረው ወንድማችን የሆነው እና የቢላል ሬዲዬ ጋዜጠኛ የነበረው ፣ ከአመት በፊት በረመዳን ወር መግቢያ ላይ በ3ተኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ የነበረው ጋዜጠኛ ካሊድ ሙሃመድ በዛሬው እለት የፈጅር ሰላቱን ሰግዶ ወደ ቤቱ በሚመለስበት ወቅት በደህንነት ሀያሎች ታፍኖ እየተደበደበ ወዳልታወቀ ቦታ ተወስዷል። ከቤቱ ውስጥም ላፕቶፖችን ጨምሮ በርካታ የሚገለገልባቸውን ንብረቶች እንደተወሰደበት ለማወቅ ተችሏል።
ወንድማችን ካሊድ በአሁኑ ወቅት የ2 ወር ልጅ ያለው ሲሆን በዛሬው እለት የደህነነት ሀይሎች በአራስ ባለቤቱ ላይም ከፍተኛ ድብደባ እንደፈፀሙ ለማወቅ ተችሏል።
በከፍተኛ የደህንነት ሃይሎች የሚመራ የእስር ዘመቻ በሙስሊሞች ላይ መከፈቱ ተገለፀ
ከ800 -1000 የሚደርሱ ሰዎችን በአዲስ አበባ ለማሰር ታቅዷል፡፡
ፍትህ ራዲዬ /ዕለተ ረቡዕ የካቲት11/2007- በከፍተኛ የኢትዬጲያ መንግስት የደህንነት ሃይሎች የሚመራ ዘመቻ በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ መከፈቱን የፍትህ ራዲዬ የውስጥ ምንጮች አስታወቁ፡፡
ዘመቻው የተጀመረው በቀጣይ ሃገራዊ ምርጫ ላይ በህዝበ ሙስሊሙ መካከል ትልቅ ንቅናቄ ይፈጥሩብናል በሚል የሚሰጓቸውን ሰዎች በማሰር እንደሆነ ታውቋል፡፡
በሃገሪቱ የሚንቀሳቀሱ የነበሩ ፖለቲካ ፓርቲዎችን እርስ በእርስ እንዲከፋፈሉ በማድረግ የማዳከም ስራ የሰራው መንግስት ፖለቲካ ፓርቲዎቹ በአሁኑ ወቅት ለኢህአዴግ ስጋት ሊሆኑ የሚችሉት በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ ብቻ በመንጠላጠል በመሆኑ በሙስሊሙ ማህበረሰብ ዘንድ የመጨረሻ የማዳከም ዘመቻ ሊከፈትበት እንደሚገባ በማመናቸው አዲስ ዘመቻ በመላው ሃገሪቱ በሚገኙ ከተሞች ላይ በሚኖሩ በሙስሊሞች ዘመቻው መጀመሩን የፍትህ ራዲዬ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
በተለያዩ የኦሮሚያ ክልሎች የአሰሳ እና ስምሪት ተግባር እየተካሄደ ሲሆን በአዲስ አበባም በርካታ ሙስሊሞች የማሰሩ ዘመቻ ተጠናክሮ መጀመሩ ታውቋል፡፡ በሙስሊሙ ትግል ውስጥ ንቁ ተሳትፎ ያደርጋሉ ተብሎ የሚታሰቡ ሰዎችን በሙሉ ወደ እስር ቤት ለማስገባት የተወሰነ ሲሆን ይህንንም ዘመቻ በጅማ እና በአዲስ አበባ እየተተገበረ መሆኑ ታውቋል፡፡
ይህ ዘመቻ የሚመራው በከፍተኛ የደህንነት ሃላፊዎች መሆኑ የተገለጸ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በአዲስ መልኩ በተዋቀረ ና በተደራጀ ሁኔታ የሙስሊሞችን እንቅስቃሴ በመከታተል ንቁ ተሳትፎ ያደርጋሉ ተብሎ የሚታሰቡ ሰዎችን ወደ እስር ቤት የማጎር ዘመቻ እየተካሄደ እንደሚገኝ የፍትህ ራዲዬ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ሃገር አቀፍ ምርጫ ከመካሄዱ በፊት ቁጥራቸው ከ 800 እስከ 1000 የሚደርሱ በአዲስ አበባ ከተማ የሚኖሩ ሰዎችን ለማሰር እቅድ የተያዘ ሲሆን ምርጫውን ለማደናቀፍ ከምርጫው በፊት ህዝባዊ አብዬት ለመቀስቀስ ሲንቀሳቀሱ ነበር በማለት ለመወንጀል መታቀዱን ምንጮች ለፍትህ ራዲዬ ገልፀዋል፡፡
ይህንንም ተከትሎ በዛሬው ዕለት በርካታ ቁጥር ያላቸው ሙስሊሞች ከያሉበት እየታደኑ እየታሰሩ እንደሚገኙ የፍትህ ራዲዬ ባልደረቦች ዘግበዋል፡፡
የራዲዬ ቢላል ጋዜጠኛ የነበረው ካሊድ መሐመድን ጨምሮ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቀ በርካታ ሙስሊሞች ከያሉበት በደህንነት ሃይሎች እየታፈኑ ወደ እስር ቤት እየተወሰዱ መሆናቸው ታውቋል፡፡
ሙስሊሞቹ በተያዙበት አካባቢ በወደሚገኙ የፖሊሰ ጣብያዎች እየታጎሩ ሲሆን የመኖሪያ ቤታቸውም በፖሊሶች እና በደህንነቶች እየተፈተሸ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡በመኖሩያ ቤታቸው የሚገኙ የተለያዩ ላፕቶፕ እና የግል ንብረቶቻቸው በደህንነት ሃሎች በፍተሸው ወቅት ለምርመራ በሚል መወሰዳቸው ታውቋል፡፡