âá áľá á°ááá á°áá á ááłáłáâ – ááľáá ááá?
“ደርግን የሚያህል ጠላት ከፊት ለፊታችን እያለ እንዴት እርስ በርስ በመጣላት ጊዜ እናባክናለን? ነጻ ስንወጣ የሕወሓት ፖሊሲና ፕሮግራም ሁሉንም ነገር ይፈታዋል::” ብለን ተውነው ይላሉ፡፡
በኋላ ላይ ደግሞ ሕወሓትን ስለመለወጥ ሲጠየቁ ‹‹ሕወሓት ከዚህ በኋላ የሚለወጥ ድርጅት አይደለም አርጅቷል፡፡ 40 ዓመት በኋላ የድርጅት ባሕሪይ አይቀየርም›› ሲሉ ይከራከራሉ፡፡
የትኛው ጠላት? የትኛው ትልቁ ዓላማ?
“ትልቁ ዓላማ”ና ትርጉሙ
እኔ እንዳስተዋልኩት ተቃውሞው ጎራ ያሉ አብዛኛው ቡድኖች ከሚስማሙባቸው ጉዳዮች አንዱ መንግሥት ማንኛውንም ተቃራኒ ድምፅ ለማፈን ጥረት ማድረጉን ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ይህንን ስርዓት ለመቀየር (ትልቁ ዓላማ) ሲባል እርስበርስ የሚፈጠሩ ክፍተቶችን መተው/ማለፍ እንደሚገባ ነው፡፡ ይህ ያልተጻፈ የመግባቢያ ሐሳብ በሕዝቡም በፓርቲዎችም በግለሰቦችም ውስጥ ሰርፆ በተቃውሞ ቡድኖች መካከል ልዩነቶች በተፈጠሩ ቁጥር ሕዝቡንም የሚያስከፋው “እነዚህ እርስ በርስ መስማማት ያልቻሉ እንዴት ነገ መንግሥት ይሆናሉ?” “ እንዴት በዚህ ጊዜ እንኳን ለትልቁ ዓላማቸው ሲሉ ችግሮቻቸውን አያመቻምቹም?” የሚሉት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ጉዳዩን ከላይ ከላይ ያየነው እንደሆነ የሚረባ ጠንካራ ፓርቲ አለማግኘት የማንኛውም ሕዝብ የተስፋ መቁረጥ ምንጭ ሊሆንበት ይችላል፡፡ ስለዚህ ጠንካራ ፓርቲዎችን ለማየት መመኘትና ደካማ የሚያስመስሉ ችግሮችን መሸሽም ተገቢ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን መጀመሪያ ትልቁ ዓላማችን አገራችንን ዴሞክራያዊ የተሻለች አገር ማድረግ ነው ወይስ መንግሥትን መቀየር ብቻ? መንግሥትን መቀየር የተሻለ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለማምጣት አስፈላጊ ነው ብዬ ባምንም ይህንን የምናደርገው ለወደፊትዋ ዴምክራሲያዊት ኢትዮጵያ የሚስፈልጉ እሴቶችን በመሸርሸር መሆኑ ግን ያሳስበኛል፡፡ ከነዚህ መሸርሸሮች አንዱ ደግሞ ልዩነትን እንደአማራጭ ያለመቀበል አዝማሚያ ነው፡፡ በመሆኑም አሁን ባለን የተዛባ የመቻቻልና ተስፋ ያለማስቆረጥ ጽንሰ ሐሳብ ከቀጠልን እንደአገር በዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ ውስጥ የምናጣው ነገር ከመብዛቱም በተጨማሪ የሚመጣው ስርዓት የተሻለ ለመሆኑ ማረጋገጫ አይኖረንም ብዬ እከራከራለሁ፡፡
ለ”ትልቁ ዓላማ” ሲባል ቅድሚያ የሚሰጣቸው የማይመስሉ ነገሮችን መሸፋፈን ባሕላችን እስከዛሬ ውጤታማ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ ይህ የአለባብሶ የማረስ ትብብር በአረም ሲያስመልሰን ብዙ ጊዜ አስተውለናል፡፡ እየተሸፋፈኑ የማለፍ ፖለቲካ ከውስጥ ፓርቲ ጀምሮ እስከ አገሪትዋ ወሳኝ የፖለቲካ ጊዜያት ድረስ ብዙ ጊዜ ዋጋ ሲያስከፍለን ቆይቷል፡፡ እነዚህ ያልተተቹ ያልተፈተሹ እርስ በርስ መተባበሮች መካከል በተወሰነ መልኩም ቢሆን ለምርጫ 97 ውድቀት አስተዋእፆ ማድረጉ የሚታወስ ነው:: ለ”ትልቁ ዓላማ” ሲባል የሚደረጉ ያልተጠኑ መስማማቶች “ለትልቁ ዓላማ” ሲባል የታለፉ ልዩነቶች ምርጫ 97ትን የሚያህል ስኬት ለማጣት አስተዋፅዖ አድርገዋል፡፡ስለዚህ ለ”ትልቁ ዓላማ” ሲባል የሚታለፉ ልዩነቶቸ መጨረሻውን ውጤት ስኬታማነት ስለሚቀንሱት ለምንድነው የምንተባበረው? ከነማንጋር ነው አብረን መሥራት የምንችለው? የሚለውን ነገር ማጣራትና ልዩነትን በግልጽ ማስቀመጥ ከማይዘልቅ መተባር የተሻለ ለወደፊቱ ለፓለቲካ ባሕል ጥቅም ይኖረዋል፡፡ አሁን ባለን አካሄድ የመተባበር ሙከራዎቹ ችግሩንም ጭንቀቱንም ከመቀነስ አንጻር የሰጡት ጥቅም አይታየኝም፡፡ እነደውም ደካማ ተስፋ እየሰጡ እርሱንም በአጭሩ እያከሰሙት ብልጭ ድርግም የምትለው የተቃውሞ ፓለቲካ ላይ ተስፋ ለማሳጣት ዋነኞቹ ምክንያቶች ናቸው፡፡
የአብዛኛዎቹ የዚህ ክርክር ደጋፊዎች የምናስቀድመው “ትልቁን ዓላማ” መሆን አለበት ከማለት በተጨማሪ ጊዜንና ቅድሚያ አሰጣጥን እንደተያያዥ ምክንያች ያነሳሉ፡፡ እነዚህ ምክንያቶች በቂ ሆነው ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት፣ የግለሰቦች መብት በቀላሉ ይጣሳል፡፡ ይህ ባሕል ደግሞ በየቦታው የምናነሳቸውን እሴቶች ተቃራኒ የመሆንን እና ተደራራቢ መመዘኛዎችን የመጠቀም ያጋልጠናል፡፡ የምንቆምላቸው እሴቶች ለእኛ ዓላማ ሲሆን የሚሸረፉ፣ ሌሎች ሲያደርጉት የሚያስወቅሱ ከሆነ ምኑን ቆምንላቸው?
ማስታወሻ፡- “ትልቁ ዓላማ”- The bigger picture የሚለውን የእንግዘኛ ቃል ተክቶ የገባ ነው፡፡




