በቄሮ ምንነት እና “ድርጊቶች” ላይ በርካታ ውዝግቦች እየተነሱ ነው። ውዝግቦቹ የሚነሱት በሁለት ፅንፎች ነው፦ ፩ኛው ፅንፍ ያሉት ሰዎች “ቄሮ ቅዱስ ነው” ሲሉ፣ ፪ኛው ፅንፍ ያሉት  ሰዎች ደግሞ “ቄሮ እርኩስ ነው” ይላሉ። እኔ ደግሞ ቄሮ እኛ ነህ የምንለውን ይሆናል ባይ ነኝ።

እንደኔ እንደኔ የውዝግቡ ሁሉ መንስዔ የቄሮን ምንነት እና የንቅናቄውን ዓይነት፣ እንዲሁም “የትግሉን” ወይም ደግሞ “የድሉን” ባለቤት ካለመረዳት የመጣ ነገር ይሆን ይሆናል በማለት ነው ይህንን ጽሑፍ ለአማራጭ አስረጅነት ያዘጋጀሁት። እግረመንገዴንም ለውዝግቡም ይሁን ለውዝግቡ መንስዔ የሆኑ ተቃርኖዎችን እዳስሳለሁ። ዓላማዬ ከፅንፉ እና ከፅንፉ ወዲህ ዓለም እንዳለ ለማሳየት እንጂ መሞከር ብቻ ሳይሆን ፍረጃችን ተፅዕኖ እንዳለው ማስታወስም ጭምር ነው።

ቄሮ – ሥያሜው ምን ይነግረናል?

‘ቄሮ’ ቃሉ ‘ያላገባ፣ ያልወለደ’ ወጣትን ይወክላል። ነገር ግን ወጣት የሚለውን ቃል የሚተኩ ሌሎች የኦሮምኛ ቃላት አሉ። እነዚህም ‘ደርደሩማ’፣ ‘ደርገጌሳ’ እና ‘ጎሮምሳ’ የሚሉት ቃላት ምሳሌ ይሆናሉ። ቄሮ የሚለው ቃል ምንጩ ‘ቄረንሳ’ ከሚለው እና ነብር የሚል ትርጉም ካለው ቃል የተቀዳ እንደሆነ ይነገራል። ስለዚህ ቄሮ ማለት እንደነብር ያለ ብርቱ ወጣት ማለት ነው፣ ማለት እንችላለን። ይሁን እንጂ አሁን በተለይ በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ ‘ቄሮ የሚለው ቃል ፍቺ ‘አብዮተኛ ወጣት’ የሚል ትርጉም አለው።

“የቄሮ ንቅናቄ” ውልደት እና ዕድገት

ቄሮ የሚለው ቃል የፖለቲካ መድረኩ ውስጥ የገባው እ.ኤ.አ. በ2011 የአረቡ አብዮት በፈነዳበት ወቅት ነበር። መቀመጫውን ዳያስፖራ ያደረገው ንቅናቄ ከዩንቨርስቲ ተማሪዎች ጋር ግንኙነት በመመሥረት ‘ቄሮ ቢሊሱማ ኦሮሞ’ የሚባል ኢመደበኛ ማኅበር ፈጠረ። የዚህ ማኅበር አባላት መረጃዎችን በኢሜይል እና በድረገጻቸው እየተለዋወጡ በርካታ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ ቀጠሉ። ሥማቸው በይፋ የተነሳው ግን በ2006 የአዲስ አበባ ከተማ ማስተር  ፕላንን ተከትሎ በተነሳው እና ዩኒቨርስቲዎችን ባዳረሰው የተቃውሞ ሰልፍ ወቅት ነው።

ከዚያ በኋላ የተጋጋለው የተቃውሞ ሰልፍ መላው ኦሮሚያን ሲያዳርስ በየአካባቢው ያሉ ወጣቶች ራሳቸውን ቄሮ ብለው መጥራት ጀመሩ። የመጀመሪያው የቄሮ አደራጅ የነበረው (qeerroo.org የተባለ) ድረአምባም ይሁን የፌስቡክ ገጹ አሁን እምብዛም ተከታታይ የላቸውም። ይልቁንም የወጣቶቹ ኅብረት መሪ ተደርጎ በዘልማድ የሚወሰደው የኦኤምኤን ቴሌቪዥን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጃዋር መሐመድ ነው።

ከዚያ በኋላ በኦሮሚያ ክልል፣ በየአካባቢው የሚነሱት ተቃውሞዎች ውስጥ የሚሳተፉ የተደራጁም ይሁኑ ያልተደራጁ ወጣቶች በሙሉ – ራሳቸውን ሲገልጹም ይሁን ሌሎች ሲገልጿቸው – ቄሮ በሚል ሥያሜ ሆነ። ቄሮ በዚህ አካሔድ በማንም ግለሰብ ወይም ቡድን ቁጥጥር ሥር ያልሆነ፣ ነጻ ነገር ግን በኦሮሙማ (ኦሮሞነት) የተሰባሰበ ኢመደበኛ ቡድን ሆነ። ይህ ማለት ግን ወጣቶቹ በፖለቲካ ፍልስፈፍናቸውም ይሁን ብስለታቸው፣ በኢትዮጵያ እና ኦሮሚያ ታሪክም ይሁን ፖለቲካ አረዳዳቸው ወጥ አቋም አላቸው ማለት አይደለም።

ይህ በእንዲህ እያለ በአማራ ክልል የነበረው ሕዝባዊ ተቃውሞ ላይ የሚሳተፉትን ወጣቶች ሥም ለመስጠት ተሞከረ። ‘ፋኖ’ የሚለው ሥያሜ ‘ቄሮ’ ከሚለው ጎን ለጎን መጠቀሱ የተለመደ ነገር ሆነ። ያን ጊዜ በቄሮ ሥምም ሆነ በፋኖ ሥም የሚደረገው ነገር በሙሉ፣ ማዕከላዊ መንግሥቱን እስካስጨነቀ ድረስ “ትክክል” ነበር። ይሁን እንጂ መሬት ላይ “ቄሮ ነኝ” የሚሉትን ያክል፥ “ፋኖ ነኝ” የሚሉ ወጣቶች እምብዛም አልነበሩም። እንዲያውም ‘ፋኖ’ የግንቦት ሰባት ፈጠራ ነው የሚሉ የአማራ ብሔርተኞች ገጥመውኛል። ይሁንና የመንግሥት ባለሥልጣናት ሳይቀሩ አሁን ለምናየው የለውጥ አዝማሚያ አስተዋፅዖ ያበረከቱ ወጣቶችን ሲጠሩ “ቄሮ፣ ፋኖ፣ ዘርማ…” እያሉ መጥራትን ‘ፕሮቶኮል’ አድርገውታል።

የትግሉ እንዲሁም የድሉ “ባለቤቶች”

የያኔዎቹ ኦሕዴድ እና ብአዴን ተባብሮ ትሕነግ ላይ ማበይ፥ ከወጣቶቹ አመፅ ባልተናነሰ (ወይም በበለጠ መልኩ) ኢሕአዴግን ነቀነቀው። የፓርቲዎቹ ከወጣቶቹ ጋር ያልተጻፈ መግባባት ላይ መድረስ ደግሞ የቀድሞውን ኢሕአዴግን ገድሎ፣ አዲሱን ኢሕአዴግ ወለደ። አሁን ከትሕነግ/ኢሕአዴግ ወደ ኦዴፓ/አዴፓ/ኢሕአዴግ አገዛዝ ተሸጋግረናል። ይሁንና ገና አመፁ አልሰከነም። የትግሉ ባለቤት ተቃዋሚዎች በሙሉ፣ በተለይም አደባባይ የወጡት የኢትዮጵያ ወጣት አመፀኞች ናቸው፤ የድሉ ባለቤቶች ግን የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች፣ በተለይም ኦዴፓ እና አዴፓ ናቸው። ያለእነሱ ከቀድሞ አቋማቸው መቀልበስ፣ እንዲሁም ለማበር መወሰን በኢሕአዴግ ቤት አሁን ያለው ወደ ዴሞክራሲ የመሸጋገር ዕድል ፈፅሞ አይመጣም ነበር ብዬ እገምታለሁ።

ይሁንና ወጣቶቹ የልኂቃን ተቃዋሚዎችን ጥያቄ ከማስተጋባት ባሻገር ለእንዲህ ያለ ነፍስን አሳልፎ እስከመስጠት የሚደርስ ብሶት የዳረጋቸው ሥራ አጥነት እና ‘የሪከግኒሽን’ ጥያቄ መልስ ቢሰጠው ኖሮ፥ ድሉን የጋራ ድል አድርገን መቁጠር የምንችልበት ዕድል ይኖር ነበር።

አሁን ባለው ሁኔታ ብዙኃን ሥራ አጦች በየአደባባዩ በከፈሉት መስዋዕትነት፥ ‘እነዚህ ሥራ ፈቶች ደግሞ መረበሽ ጀመሩ’ እያሉ ይበሳጩባቸው የነበሩ ልኂቃን በአንድ በኩል፣ እንዲሁም በሌላ በኩል ደግሞ ‘እስከመቼ እንዲህ ተዋርዳችሁ ትኖራላችሁ፣ ታግላችሁ ነጻ ውጡ እንጂ’ እያሉ ሲቆሰቁሷቸው የነበሩ ልኂቃን ሥልጣን እየተቆጣጠሩ ሲመጡ ወጣቶቹ ችላ መባላቸው ሐቅ ነው።

ይህ ነገር ምናልባትም የትግሉ “ባለቤቶች” እና የድሉ “ባለቤቶች” ወይም “ተጠቃሚዎች” መካከል መቃቃር ሳያስከትል አይቀርም። ይህ ጉዳይ አዲስ ብሶት የሚወልድ መሆኑም የጊዜ ጉዳይ ነው።

“ጀግኖች” የነበሩ “ፅንፈኞች”
(የውክልና ጦርነት መሣሪያዎች)

በየአካባቢው በሥራ አጥነታቸው ምክንያት ዋጋ አጥተው፣ በአደገኛ ቦዘኔነት ተፈርጀው ከፊሉ ስደት እየበላቸው፣ ከፊሉ ሱስ እየዋጣቸው የነበሩ ወጣቶች ድንገት የተቀጣጠለው ሕዝባዊ አመፅ ማገዶ ነበሩ። ያኔ “ጀግኖች” ተብለዋል። ምክንያቱም ለልኂቃኑ ፖለቲካ ሁነኛ መሣሪያ ነበሩ። ወጣቶቹ ምናልባትም አእምሮ ከሚያላሽቅ የሥራ አጥነት ስሜት ወጥተው፥ ለራሳቸው ያላቸው ዋጋ እና ግምት የጨመረው በዚህ አመፅ ባደረጉት ተሳትፎ ይሆናል። ሕዝባዊ አመፁ ቆሞ ድንገት አገር መረጋጋት ሲጀምር ግን ወደ “መንደር ያሰለቹ አደገኛ ቦዘኔነት” መመለሳቸው ሆነ። ከተሰጣቸው ሥም መውረድ ከባድ ነው። ስለሆነም የአብዮታቸው ጠባቂ ሆኑ – ከሳሽ፣ ፈራጅ እና ቀጪ። የደቦ ፍርድ፤ በዚህ ወቅት ነው በፅንፈኝነት መፈረጅ የጀመሩት።

በዕውቁ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የምትመራው ‘ኢትዮጲስ’ ጋዜጣ (በጥቅምት 24, 2011 እትሟ) በርዕሰ አንቀፅዋ ቄሮዎችን ለዘብተኛ እና ፅንፈኛ በሚል ከለያየቻቸው በኋላ ፅንፈኞቹን የማስቆም ሥራ መሠራት እንደሚገባ ጠቁማለች። የኢትዮጲስ ስህተት ምናልባት (አንድም) በአገሪቱ የደቦ ፍርዶች እና ወደ ስርዓት አልበኝነት የሚወስዱ እንቅስቃሴዎችን ለቄሮ ብቻ ለይታ መስጠቷ ነው። መቼም በድንጋይ ወግሮ መግደል እና በእንጨት ላይ ዘቅዝቆ መስቀልን የመሳሰሉ የደቦ ፍርዶች አንዱ ከሌላው የሚሻሉበት መንገድ አለ ተብሎ አይታመንም። በዚህ ረገድ ጉዳዩ ‘ወጣት ፅንፈኞች’ በሚል ሊጠቃለል ይችል ነበር ብዬ አምናለሁ። (ሁለትም) ቄሮ የተጻፈ ፕሮግራም የሌለው፣ አባላቱ በዝርዝር የማይታወቁ፣ አንድ ስትራቴጂ እና ግብ የሌለው የግፉአን ማኅበር መሆኑን ከግምት ውስጥ ያላስገባ መደምደሚያ መሆኑ ስህተት ያደርገዋል። ይህም ማለት ማንም ተነስቶ ቄሮ ነኝ ብሎ ማወጅ እና በዚያ ሥም ወንጀልም ይሁን መልካም ጀብዱ መፈፀም ያስችለዋል ማለት ነው። ብዙኃን መገናኛዎች ግን ቡድኑን ግልጽ ቅርፅ እና መዋቅር እንዳለው እንዲሁም “ተግባሩን” አቅዶ እንደፈፀመ ማኅበር ተመልክቶ “እንዲህ ነው” ወይም “እንዲያ ነው” ማለት የተሳሳተ ትርጉም ይሰጣል። (ሦስትም) የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች – ለምሳሌ የጃዋር “የቄሮ መንግሥት” እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ “ፀጉረ ልውጦችን መቆጣጠር” የመሳሰሉ – ንግግሮች ወጣቶቹን የውክልና ጦርነት ውስጥ እንደከተታቸው ከግንዛቤ ያላስገባ መደምደሚያ መሆኑ ነው።

ፍረጃ እና ተፅዕኖው፤
እስመ ሥሙ ይመርሖ ሀበ ግብሩ
(nomen est omen)

ቄሮንም ይሁን ፋኖን ወይም ሌላ የፖለቲካ ቡድኖችን በተመለከተ ለምናደርጋቸው ፍረጃዎች ማድረግ የሚገባን ጥንቃቄ አለ። ፍረጃ (labeling) በሥነ-ልቦና ግንባታ የሚያሳድረው ተፅዕኖ እንዳለ በርካታ ጥናቶች ያሳያሉ። «እነ እከሌ ይህን አያደርጉም»፣ «እንትን ሆኜ እንዲህ አላደርግም» የሚሉ አባባሎች የሚያስረዱን ቁምነገር ቢኖር የሆኑ ሰዎች ስብስብን የሚገልጽ ማንነትን የምንበይንበት (labeling/defining) መንገድ መልሶ የአባላቱን ድርጊት እንደሚወስን መረዳት እንደሚያሻን ነው። “ቄሮ አብዮተኛ ወጣት ነው” በተባለ ጊዜ አደባባዮችን በተቃውሞ ሰልፎች ንጧል። የለውጥ ጀምበር ሲከፈት “ለውጡን ጠብቁ” ሲባል እንደዚያው ለማድረግ እየሞከረ ነው። ወጣቶቹ በልኂቃኑ የሚሰጣቸውን ሥያሜ ለመመጠን እየተፍጨረጨሩ ነው። “ቄሮ መንግሥት ነው” ብለን ከአቅሙ በላይ ሥራ ከምናሸክመው፣ “ቄሮ የዴሞክራሲ እና የሥልጡን ፖለቲካ ጠበቃ ነው” ብለን በዚህ አቅጣጫ እንዲተጋ ብናደርገው ይመረጣል። “ቄሮ ፅንፈኛ ነው” እያልን ወደዚያ ከምንገፋው “ቄሮ ይህንን አያደርግም” ብለን ብንገስፀው ይሻላል።

ቺርስ ለጥንቃቄ!

ትላንት አንድ የስዊድን ጋዜጠኛ “ሐሳብን ከመግለጽ ነፃነት ይልቅ ደኅንነቴን እመርጣለሁ” የሚል አስተያየት አዲስ አበባ ላይ እንደገጠማት ነገረችኝ። ዛሬ ደግሞ በጥዋቱ አንዲት አሜሪካዊ ጓደኛዬ በዋትሳፕ “ብጥብጥ ካለበት ዴሞክራሲ ይልቅ ሠላማዊ አምባገነንነት ይሻላል” የሚል ክርክር እንደገጠማት ነገረችኝ። በጣም ነው ያዘንኩት፤ ምክንያቱም እዚህ ድምዳሜ ላይ እንድንደርስ የሚፈልጉ የፖለቲካ ቡድኖች እንዳሉ አውቃለሁ።

በመሠረቱ ዛሬ በጉዳዩ ላይ በአጭሩ መሞነጫጨር የፈልግኩት በነዚህ ሰዎች ብቻ አስተያየት ተነሳስቼ አይደለም። “ጭቆና ለምደን ነፃነት መሸከም አቃተን” የሚሉ አስተያየቶችን ደጋግሜ እሰማለሁ። ስህተቱ የሚጀምረው ዴሞክራሲም ይሁን ነፃነት ላይ “ደርሰናል” ከሚለው ድምዳሜ ነው። አሁን ያለንበት ሁኔታ ዴሞክራሲያዊ ነፃነት ለማዋለድ በምጥ ላይ ነው ቢባል ይሻላል። እንደ አዋላጆቹ ብቃት ፅንሱ (ዴሞክራሲው) ይወለዳል ወይም ይጨናገፋል። አዋላጆቹ ካላወቁበት ደግሞ ፅንሱ እናትየውን ጨምሮ ይዞ ሊሔድ ይችላል። ስለዚህ ድምዳሜያችን ጥንቃቄ የሚያሻውን ጉዳይ ችላ እንድንለው ሊያደርገን ይችላል። ግን ዋነኛው የአረዳድ ችግር የዚህ ጉዳይ ብቻ አይደለም።

ሠላም በአምባገነንነት እና በዴሞክራሲ ውስጥ

አምባገነንነት ሕዝቡ “በቃኝ” ብሎ ቀና እስከሚል ድረስ ረግጦ የመግዛት ስልተ መንግሥት ነው። አምባገነኖች የበቃኝ ነጥብ ከመድረሷ በፊት ሁሉንም ነገር ስለሚያፍኑ ሠላም ያለ ያስመስላሉ። በአምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ ፀጥታ ስላለ ሠላም ያለ ይመስላል። ነገር ግን የታፈነ አመፅ አለ፤ የታፈነ ደም መፋሰስ አለ። ስለ አመፁም ይሁን ስለ ደም መፋሰሱ መነጋገር አይፈቀድም። የመረጃ ምንጮችም ይታፈናሉ። በአምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ የአመፁ መሪ መንግሥት ነው።

በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግን ሰዎች ቅሬታቸውን ሁሉ ያጮኻሉ፣ ትንሿም ብሶት ሳትቀር ትሰማለች። ይህ ራሳቸውን እንደሰጎን አሸዋ ውስጥ ቀብረው የሚኖሩትን ብዙዎች ከምቾት ዞናቸው ስለሚያስወጣቸው ሠላም ደፈረሰ ይላሉ። በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ፀጥታው ይደፈርስ ይሆናል እንጂ እንደ አምባገነናዊ ስርዓት ሠላም አይደፈርስበትም። ግጭቶች በዴሞክራሲያዊ ስርዓትም ውስጥ አሉ። ይሁን እንጂ ንግግር ስለማይታፈን ግጭቶችን በአካል ሳይከሰቱ በድርድር መፍትሔ ይፈለግላቸዋል፤ ከተከሰቱም በኋላ በአጭሩ ለመቅጨት ፈጣን መፍትሔ ለመፈለግ ዴሞክራሲ ያስችላል።

በጣም ስኬታማ የሚባሉት አገሮች ውስጥ ልዩነቶቻቸውን በዴሞክራሲያዊ ስርዓት አቻችለው ኖረዋል፤ እኛም እንችላለን!

ሐሳብ እና አመፅ

“እመፅ ማነሳሳት” እና “የጥላቻ ንግግር” የሚባሉ ችግሮች አሉ። ነገር ግን ብዙዎች ቃላቱን የሚጠቀሙባቸው የማይፈልጉትን ሐሳብ ለማፈን ሲሆን ብቻ ነው። በመሠረቱ ዓለም ዐቀፍ ስምምነቶች ላይ ሐሳብን የመግለፅ ነፃነት እንዲከበር ቁርጠኛ አቋም የተወሰደበት አንዱ ምክንያት ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት “አመፅ” እና “ለውጥ” መካከል ሚዛን መፍጠር ስለሚችል ነው። ሐሳባቸውን በነፃነት እንዲገልፁ ያልተፈቀደላቸው ሰዎች በአመፅ ያደርጉታል። እንዲናገሩት ሲፈቀድላቸው ግን የሚጋጩ ፍላጎቶቻቸውን ሳይቀር ማስታረቂያ መንገድ በመነጋገር ይፈልጋሉ።

በአገራችን መደራጀትም ይሁን ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት ታፍነው መኖራቸው የአደባባይ ምስጢር ነው። ይህ በእንዲህ እያለ የማኅበራዊ ሚድያ መከሰት ተናደው መድረክ ያጡትንም፣ የተስማሙ የሚመስላቸውንም የሚጋጩትንም በአንድ ግንባር አገናኛቸው። በዚህ መሐል ጎራ ለይተው በሐሳብ መቆሳሰላቸው የሚጠበቅ ነው። መሬት ላይ ለመግባባት መነጋገርን፣ የዜግነት መብት እና ግዴታዎችን ማወቅ እና ማክበርን የሚያስተምሩ ሲቪል ማኅበራት ቢያብቡ ኖሮ፥ ሐሳቦች በየጉዳዩ ላይ ዕውቀት ካላቸው ሰዎች አንደበት ተቀብለው የሚያንሸራሽሩ ሚድያዎች ቢያብቡ ኖሮ፥ ዛሬ አላዋቂዎች ባሻቸው ጉዳይ ላይ ደፋር ተንታኝ ሆነው ብዙ ተከታይ እና አድማጭ አያፈሩም ነበር። ለዚህ ያበቃን አምባገነንነት እንጂ ዴሞክራሲ አይደለም።

አሁንም ቢሆን መፍትሔው ማዕቀብ አይደለም፤ ነፃነት ነው። ሁሉም ሰዎች በነፃነት በተነጋገሩ ቁጥር አሸናፊ ሐሳቦች እየተንጓለሉ ይወጣሉ። “እውነት ለሐሰትም ሳይቀር ምስክር ነች” እንደሚባለው፥ የሚዋሹት እውነት በሚናገሩት ይጋለጣሉ፤ ጥላቻ የሚሰብኩት ፍቅር በሚሰብኩት ይሸነፋሉ።

መፍትሔው በሰው ልጅ ማመን ነው

አምባገነናዊነት እና ዴሞክራሲያዊነት በሰው ልጆች ላይ ያለን እምነት መገለጫዎች ናቸው ብዬ አምናለሁ። አምባገነን ስንሆን ሰዎች መጥፎዎች ናቸው። ቁጥጥር፣ እገዳ እና ቅጣት ያስፈልጋቸዋል ብለን እናምናለን። ዴሞክራት ስንሆን ደግሞ በተቃራኒው በሰው ልጆች ቀናነት እምነት ይኖረናል። ሰዎች ሲያጠፉ እንኳን ለክፋት ወይም ክፉ በመሆን ሳይሆን በመሳሳት ነው ያደረጉት ብለን እናምናለን። ስለዚህ ዴሞክራት ስንሆን ለሰዎች ነፃነት፣ ከኃላፊነት እና ተጠያቂነት ጋር እናጎናፅፋለን።

በዴሞክራሲ ተስፋ ቆረጥን ማለት በሰው ልጆች ተስፋ ቆረጥን ማለት ነው።

የኢትዮጵያ ሥርወ መንግሥት መነሻ ማዕከሉ (core state የሚሉት) ሰሜን ላይ ነበር – አክሱም። ቀስ በቀስ ወደ ደቡብ እያፈገፈገ በ19ኛው ክፍለ ዘመን ማገባደጃ ላይ ሸዋ ላይ ከትሞ እስከ ዛሬ ዘልቋል። ‘የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ’ በአሁኑ ቅርፅዋ የተሠራችው በ19ኛው ክፍለዘመን ማገባደጃ ነው። ከዛሬዪቱ ኢትዮጵያ በፊት የነበረችው ‘ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ’ ነች። ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እንደሌሎቹ የዓለማችን ጥንታዊ አገራት ሁሉ፣ ድንበር አልነበራትም – የተፅዕኖ አድማስ እንጂ።  የተፅዕኖ አድማሷ ደግሞ እንደ ጊዜው እና እንደ ነጋሹ አቅም ሲሰፋና ሲጠብ ነው የከረመው።


ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ የአማርኛ ተናጋሪዎች እና የትግርኛ ተናጋሪዎች በዋነኝነት የሚዘውሯት ነበረች። በተለይ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ወዲህ ያለችው ኢትዮጵያ በሁለቱ ፉክክር እና ማመቻመች (compromise) ነበር የቆመችው። ዳግማዊ ምኒልክ ደቡቡን እና ምሥራቁን የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ አካል ባደረጉበት ወቅት ግን በቁጥር ከትግርኛ ተናጋሪዎቹ እና ከአማርኛ ተናጋሪዎቹ የሚበልጡ ኦሮሞዎች የአገረ መንግሥቱ አካል በመሆናቸው፥ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች በፊት ከነበራቸው ተቀናቃኝነት የበለጠ ኃይል አግኝተዋል። ይህ ክስተት ኢትዮጵያን ሦስተኛ የሥልጣን ተፎካካሪ እንድታገኝ አድርጓታል። (ይህ ማለት ግን ከዚያ በፊት ኦሮሞዎች የአገረ መንግሥቱ አካል አልነበሩም ማለት አይደለም፤ ሸዋ ቀድሞውንም ቅይጥ ከመሆኑም ባሻገር፣ በ16ኛው ክፍለ ዘመን ‘ታላቁ የኦሮሞ ፍልሰት’ የኦሮምኛ ተናጋሪዎች ሰሜኑን የኢትዮጵያ ክፍል ተቀላቅለዋል። ይህም የወሎና የጁ ኦሮሞ ፖለቲከኞችን አፍርቷል። በዘመን ወደኋላ በነጎድን ቁጥር ታሪኩ ይለዋወጣል፤ ስለዚህ ርቀን ባንሔድ ጥሩ ነው። የዚህ ጽሑፍ ዓላማም ዛሬን በሚጫኑ የቅርብ ጊዜ ታሪካዊ መቀናቀኖች ላይ ማተኮር ብቻ ነው። እንዲያውም ትግራይን ከተፎካካሪ ሕዝቦች የነጠሉ የታሪክ ኩነቶችን መለየት ነው።)

የኤርትራ (ባሕር ምላሸ) የጣልያን ቅኝ ግዛት መሆን የትግራዋዩን ቁጥር በግማሽ ቢቀንሰውም ትግራይ የመንግሥት መነሻ ማዕከል በመነበሯ ምክንያት የመሐል አገር የሥልጣን ፉክክሩ ውስጥ ተፅዕኖዋ ሳይቀንስ ከርሟል። በዳግማይ ምኒልክ ሰዐት ትልቁ ኃይል እና ሥልጣን ሸዋ ላይ ተከማችቶ የነበረ ቢሆንም፣ ትግራይ እና ደቡቡም በየአካባቢ ንጉሡ የተወሰነ ነጻነት ነበረው። በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ (ቀኃሥ) ግዜ ግን የአካባቢ ነገሥታት ሁሉ ከስመው ማዕከላዊነት ሰፈነ። ቀኃሥ የሥልጣን መስህቡን ሁሉ አዲስ አበባ ላይ – በመዳፋቸው ሥር አኖሩት።

ደርግም የቀጠለበት ይህንኑ የቀኃሥ እጅግ የተማከለ መንግሥታዊ ስርዓት ነው። ኢሕአዴግ ሲመጣ ምንም እንኳን በፌዴራል ስርዓት የማዕከላዊ መንግሥቱን ሥልጣን በሕግ (de jure) ለክልሎች ቢያከፋፍልም በተግባር (de facto) ትልቁ ሥልጣን ግን በማዕከላዊ መንግሥቱ ቁጥጥር ሥር ነበር። የኢሕአዴግ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት በእጅ አዙር የሥልጣኑን ቁጥጥር ለኢሕአዴግ ፈላጭ ቆራጮቹ ትሕነግኦች (TPLFs) ስላጎናፀፈ መቐለን ከአራት ኪሎ ያላነሰ ባለ ሥልጣን አድርጓት ነበር።


የትግራይ ፖለቲከኞች የማዕከላዊ ፖለቲካውን ለመቆጣጠር ባደረጉት ትግል፥ የኤርትራ ትግራዋዮች ድጋፍ አስፈልጓቸው ነበር። ይሁን እንጂ የትሕነግ ፖለቲካ ቢያንስ በሕግ ደረጃ ክልሎችን የሚያጠናክር በመሆኑ መልሶ ራሱን በልቶታል። ቀድሞ ያልነበሩ የኦሮምያ እና የአማራ ክልሎች ባለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት የራሳቸው መንግሥታዊ መዋቅር፣ የራሳቸውን የፀጥታ ኃይል እና አስተዳደራዊ መዋቅሮች ዘርግተው አንድ ትውልድ ሲያሳልፉ የሕዝብ ቁጥራቸውን የሚያክል ጥያቄ ይዘው ተነሱ። የትሕነግ ሰዎች የፌዴራሊዝሙን ፅንሰ ሐሳብ ሲነድፉ ወቅታዊ የበላይነታቸውን እንጂ ዘላቂ ውጤቱን የጠረጠሩ አይመስለኝም። አሁን ወደ ዳር የመገፋታቸውን ውጤት መቀበል ሲያዳግታቸው በማየቴ ይህንን አልኩ እንጂ፥ ምናልባት ሲጀምሩት አግባብ ነው ብለው አምነውበትም ሊሆን ይችላል። የሆነ ሆኖ አሁን በግልጽ እንደምናስተውለው የኦሮሞ እና አማራ ጥምረት የመንግሥትን ሥልጣን ተቆናጥጧል። ይህንን መቀልበስ የሚችል ኃይል በቅርብ ግዜ የሚመጣ አይመስለኝም።

የታሪካዊቷ ኢትዮጵያ ግዛተ ዐፄ ከተመሠረተበት ግዜ ጀምሮ አሸናፊው ተሸናፊውን እየዋጠ እዚህ የደረሰው የኢትዮጵያ አገረ መንግሥት፥ አሁን አዲስ ምዕራፍ ላይ ነው። በዶናልድ ሌቪን አገላለጽ በአማራው አንብሮ (thesis) እና በኦሮሞው ተፃርሮ (anti-thesis) የተገነባችው ‘ታላቋ ኢትዮጵያ’ (የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ብዬ ነው እኔ የምረዳው) የወትሮ የሥልጣን ተቀናቃኞቹን (የትግርኛ ተናጋሪዎቹን) ከማዕከላዊው መንግሥት ገለል አድርጎ፣ ተረኛ እና ዋነኛ ዘዋሪዎቹ ሁለቱ ድምር ብዙኃን፣ ማለትም የኦሮምኛ እና የአማርኛ ተናጋሪዎችን አንግሧል። ይህ ለጊዜው ቢጨናገፍ እንኳን ለአገራዊ ቀውስ እና አለመረጋጋት ይዳርጋል እንጂ አይፀናም።

የትግራይ ፖለቲካ የዳር አገር ፖለቲካ የሆነው በሚከተሉት ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶች ነው፦ አንደኛ የመናገሻ ከተማው ከትግራይ ተነቅሎ ወደ ደቡብ በመጓዝ በመጨረሻ ሸዋ ላይ መፅናቱ ጂኦግራፊያዊ ፋይዳዋን በመቀነሱ፣ ሁለተኛ የኤርትራ ቅኝ መገዛት የትግርኛ ተናጋሪውን ሕዝብ ቁጥር መቀነሱ እና ሦስተኛ በፌዴራሊዝሙ የኦሮምኛ ተናጋሪ እና የአማርኛ ተናጋሪ የተከፋፈሉ ክፍለ አገሮች ተቀላቅለው ብዙ ሕዝብ የያዙ (እና መደራደሪያ የሆናቸው) ክልሎች መፈጠራቸው ናቸው። እዚህ እንደምናየው በትግራይ ወደዳር መገፋት የትሕነግ ፖለቲካ የመጨረሻውን መዋጮ ማድረጉን ነው።

አሁን በሕዝብ ብዛት ሦስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙት ሶማሊዎች ናቸው። እንደምናስተውለው የሶማሊ ፖለቲካ ከጊዜ ወደጊዜ መደ መሐል (mainstream) እየመጣ ነው። በተቃራኒው የትግራይ ፖለቲካ ከመሐል ወደ ዳር (periphery) እያፈገፈገ ነው። ስለዚህ በመጪዎቹ ሁለት እና ሦስት ዐሥርት ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የትግርኛ ተናጋሪዎች የፖለቲካ ተፅዕኖ እየቀነሰ የመሔድ ዕድሉ በጣም ሰፊ ነው፤ ከትግርኛ ተናጋሪዎች ይልቅ ሶማሊኛ ተናጋሪዎች ወደ መሐል ይቀርባሉ። ከዚህ በኋላ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት በኢትዮጵያ የሚሰፍን ከሆነ በብዙኃን አመራር (majority rule) መርሕ ትልቁን ሥልጣን የሚቆጣጠሩት የኦሮምኛ ተናጋሪዎች እና የአማርኛ ተናጋሪዎች ጥምረት ነው። ይህ የፌዴራል ስርዓቱ ቅርፅ ቢቀያየርም እንኳን በተለየ መልኩም ቢሆን መቀጠሉ አይቀርም።

በሌላ በኩል፣ የኦሮምኛ እና የአማርኛ ተናጋሪዎቹ አንድ ጥምረት ለመመሥረት መስማማት ቢያቅታቸውም የመጨረሻዎቹ ሁለት ግንባሮች (frontiers) እነርሱ በመሆናቸው የዳር አገር አጋር በማፍራት በፈረቃ ጉልህ (dominant) ድርሻ እየተወጡ ይቀጥላሉ። ከሁለቱ መሐል ያልወጡ ቡድኖች ሥልጣን የሚቆጣጠሩበት እጅግ ጠባብ ዕድል ቢኖርም፥ የሁለቱን ሕዝቦች ፍላጎት እና ጥያቄ በማስተናገድ ይጠመዳሉ። የኢትዮጵያ አገረ መንግሥት ዕጣ ፈንታ ግን የሁለቱ ሕዝቦች ፍላጎት እና ውሳኔ ወዲያ ወዲህ እያላጋው ለረዥም ግዜ መጓዙ አይቀርም።

የእነዚህ ሁለት ክፈለ ዘመናት ፖለቲካዊ ሒደት በአሁኑ የኢትዮጵያ የሽግግር ፖለቲካ ተስተውሏል። የትግራይ ፖለቲከኞች የወታደራዊ አቅማቸውም ይሁን በተለያዩ ማስፈራሪያዎች የሁለቱን ብዙኃን ጥምረት ማሸነፍ አልተቻላቸውም። ለዚህ የትግራይ ፖለቲከኞች ሽንፈት የትሕነግ ራስን በራስ የሚያጠፋ ፖለቲካ የመጨረሻውን በትር አሳርፏል። ይህንን እውነት በመጋፈጥ የትግራይ ፖለቲካኞች ነባሩን የመሐል ፖለቲከኛ አጨዋወታቸውን በመቀየር የዳር አገር ፖለቲካ መጫወት ይኖርባቸዋል።

በዚህ ርዕስ ረዥም መጣጥፍ መጻፍ ከጀመርኩ ረዥም ግዜ ሆነኝ፡፡ እስካሁን አላለቀም፡፡ ምክንያቱ ግልጽ ነው፤ ጉዳዩ ስሜት የሚነካ እና በስሜት የሚነዳ ስለሆነ ፈርቼው ነው፡፡ የፖለቲካ ተዋስኦዋችንን በተከታተልኩት ቁጥር የተረዳሁት አንድ ነገር ቢኖር “ብሔርተኛ ነኝ” በሚሉ እና “ብሔርተኛ አይደለሁም” በሚሉት ሰዎች መካከል ያለው ልዩነት ብሔርተኝነትን የማመን እና የመሸሸግ ችሎታ ልዩነት ነው፡፡ ወይም ደግሞ አንዳንዴ ልዩነቱ ግለሰቦቹ የሚያራምዱት ብሔርተኝነት የሚያቅፋቸው ሰዎች ቁጥር የበዛ መሆኑ ‹ብሔርተኝነቱን› የመሸሸግ ዕድል ያገኛል፡፡ በጣም በተሳሳተ መደምደሚያ ላለመጀመር ያክል “ብሔርተኝነት” ደረጃው እና ልኩ ይለያይ ይሆናል እንጂ ሙሉ ለሙሉ ከውስጡ የወጣለት ሰው የማግኘት ዕድላችን ጠባብ ነው ብለን እንስማማ፡፡ የሆነ ሆኖ፣ ‹ብዙኃን ብሔርተኛ ናቸው› የሚል መደምደሚያ ይዤ ነው ይህንን የምር አጭር ያልሆነ መጣጥፍ፣ ረዘመብኝ ካልኳችሁ መጣጥፌ ጨልፌ እና ጨምቄ የማስነብባችሁ፡፡

የመጀመሪያው አንቀፄ እንደሚያመለክተው ‹ብዙኃን ብሔርተኞች ናቸው›፡፡ ‹ብሔርተኝነት ቅዱስ ነው ወይስ እርኩስ?› የሚል ጥያቄ ማንሳት ‹ብዙኃን ቅዱስ ናቸው ወይስ እርኩስ?› የሚል ጥያቄ እንደማንሳት ያስፈራል፡፡ ቢሆንም እንጋፈጠዋለን።

ብሔርተኝነት ሲበየን

ብዙዎቹ ዓለም ዐቀፍ ዩንቨርስቲዎች ውስጥ ያሉ ምሁራን ለብሔርተኝነት ያላቸው ንቀት የትየለሌ ነው፡፡ ንቀቱ አንድም ብሔርተኝነት ‹ማኅበራዊ ፈጠራ› (social fabrication) ነው ከሚል የመነጨ ሲሆን፣ በሌላ በኩል የሰው ልጅን ያክል ባለ ብሩሕ አእምሮ በአጋጣሚ በበቀለበት ማኅበረሰብ ብቻ መበየን ከእውነታው የራቀ ስለሚሆን ነው፡፡ የሆነ ሆኖ የብሔርተኝነት የመዝገበ ቃላት ፍቺው “ተመሳሳይ ባሕል ያላቸው ሕዝቦች ፖለቲካዊ ነጻነት መፈለግ” ወይም “በአገር በጣም የመኩራት ስሜት” ነው (P.H. Collin (2014))፡፡

ኢንሳይክሎፔዲያ ብሪታኒካ ብሔርተኝነትን የሚበይነው እኔንም በሚያስማማ መልኩ ነው፡- “የአንድ ግለሰብ ታማኝነት እና ቁርጠኝነት ከሌሎች ግለሰቦች እና ቡድኖች ፍላጎት በላይ ለብሔረ-መንግሥቱ (nation state) ማድላት ላይ የተመሠረተ ርዕዮተዓለም ነው”። በዚህ መሠረት ቀጣዮቹን ርዕሰ ጉዳዮች እያነሳን እንጥላለን፡፡

ሰዎች ለምን ብሔርተኛ ይሆናሉ?

ለዚህ ጥያቄ ቀላል መልስ እሰጣለሁ፡፡ ብዙ ሰዎች ብሔርተኛ የሚሆኑት ፈቅደው እና አቅደው ሳይሆን ባጋጣሚ ነው፡፡ አጋጣሚው የሚጀምረው ‹የት እና ከማን ተወለዱ?› ከሚለው ጥያቄ ነው፡፡ ሰዎች ብሔርተኝነትን በንባብ እና በውይይት ሊያዳብሩት ይችላሉ እንጂ የሚጀምሩት ግን በውርስ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ ብሔርተኝነት ራሳቸውን በአንድ የብሔር አባልነት የሚጠሩ ሰዎች እስኪኖሩ ድረስ አይኖርም፡፡ የሆኑ በአንድ አካባቢ የሚኖሩ እና የሚያስተሳስራቸው ማኅበራዊ አጀንዳ ያላቸው ሰዎች ራሳቸውን በአንድ ማንነት ለይተው መጥራት ሲጀምሩ ወይም በሌሎች በዚያ ማንነት መጠራት ሲጀምሩ ብሔርተኝነት ተጀመረ ማለት ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ ብሔርተኝነት በስሎ እና ጎርምቶ የሚወጣው እነዚያ ሰዎች ራሳቸውን ከሌሎች የተሻሉ እንደሆኑ ሲያስቡ፣ እና/ወይም በማንነታቸው ሳቢያ በሌሎች እየተጠቁ እንደሆኑ ሲያስቡ ነው፡፡ ብሔርተኝነት የሚጎመራው የጋራ ማንነት ላይ ጥቃት ያደርሳሉ ተብለው የሚታሰቡ የተለየ ማንነት እንዳላቸው የሚታመኑ ጠላቶች ሲኖሩ ነው፡፡

ከዚህ ውጪ ግን ብሔርተኞች በብሔርተኝነታቸው (ምርጫ) ውስጥ ጥቅማቸውን ሳይታወቃቸውም ቢሆን ያሰላሉ፡፡ ብዙ ግዜ ተጠቃሚ ከሚያደርጋቸው ስብስብ ውጪ በሆነ ብሔርተኝነት ውስጥ የታቀፉ ብሔርተኞችን አናገኝም፡፡ በርግጥ በዓለም ዙሪያ ሥር የሰደደ “የብሔርተኞች አምባገነንነት” አለ። የአንድ ዘውግ/ብሔር ብሔርተኞች በሚበዙበት አካባቢ ሌሎች ድምፆች ሁሉ ስለሚደቆሱ ፀጥ ይላሉ። ሆኖም ሰዎች የሚመርጡት የብሔርተኝነት ስብስብ የበለጠ የሚጠቅማቸውን ስብስብ ነው። ስለዚህ ሌላኛው ሰዎች ለምን ብሔርተኛ ይሆናሉ ለሚለው ጥያቄ መልስ የሚሆነው በውስጡ የሚያፈሩት ጥቅም ስላለ ነው ማለት ይቻላል፡፡

‹ብሔርተኝነት› ወ ‹አርበኝነት›

ብሔርተኝነትን የሚጠየፉ ትርክቶች ድምፅ እያገኙ ሲመጡ ራሳቸውን በአርበኝነት የሚገልጹ ሰዎች እየታዩ ነው፡፡ የሜርየም ዌብስተር መዝገበ ቃላት አርበኝነት “ከብሔርተኝነት ጋር እንደ አንድ የሚቆጠር ነገር ግን አንድ ያልሆነ ፅንሰ ሐሳብ ነው” ይላል። ብዙዎቹ የአገር ፍቅር (አርበኝነት) በብሔርተኝነት ሊቆጠር አይገባውም ብለው የሚያስቡ ጸሐፍት ‘አርበኝነት ከትውልድ ቀዬ፣ አካባቢ ወይም ስፍራ፣ ሕዝብ፣ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ፖለቲካ፣ ባሕል እና ወግ ጋር ያለ ስሜታዊ ትስስር የሚፈጥረው ተቆርቋሪ-ተከላካይነት ነው። አርበኝነት የወገኔን ጥቅም አላስነካም ባይነት ነው’ ይላሉ። ‘ብሔርተኝነት ማለት ምናልባትም አርበኝነት ልኩን ሲያልፍ ነው’ የሚሉም አሉ። ሲድኒ ጄ. ሀሪስ የተባለ አሜሪካዊ ጋዜጠኛ ‘Strictly Personal Prijudices’ በተሰኘ መጽሐፉ የተጠቀመው አገላለጽ የብዙዎቹን ንፅፅር ለማጠቃለል ይረዳል፡- “በአርበኝነት እና በብሔርተኝነት መካከል ያለው ልዩነት፣ አርበኛ አገሩ በምታደርገው ነገር ሲኮራ፣ ብሔርተኛ ግን አገሩ ምንም ብታደርግ ምን የሚኮራባት ነው፤ የመጀመሪያው የኃላፊነት ስሜት ሲፈጥር፥ የኋለኛው ግን ወደ ጦርነት የሚነዳ ጭፍን ትዕቢት ነው” ብሏል።

ነገር ግን ብሔርተኝነትን ከአርበኝነት ጋር ለይተው የማይመለከቱትም አሉ። ለምሳሌ ከፈረንሳዩ አብዮት ቀድሞ በጽሑፍ ዓለም አብዮቱን የለኮሰው ቮልቴር: “አንድ ሰው የአንዱ ጥሩ አርበኛ ለመሆን የቀሪው ሰው ዘር በሙሉ ጠላት መሆን ያለበት መሆኑ የሚያሳዝን ነገር ነው” ማለቱ ተጠቅሷል።

‹ኅብረ-ብሔርተኝነት› ወ ‹ዘውጌ-ብሔርተኝነት›

ብሔርተኝነት ብዙ ግዜ ቋንቋ እና/ወይም ሃይማኖትን ነው መሠረት የሚያደርገው፤ በእርግጥ ብዙ ጊዜ አንዱ በሌላው ይሸፈናል፡፡ ሆኖም ሌሎችም ብሔርተኝነቶች አሉ፡፡ ዶ/ር ተሻለ ጥበቡ የብሔርተኝነት ዓይነቶችን በአምስት ይከፍሏቸዋል፤ 1ኛ – የዘውግ (በተለይ ቋንቋን መሠረት ያደረገ) ብሔርተኝነት፣ 2ኛ – የኅብረት ብሔርተኝነት (ለምሳሌ በአፍሪካዊነት፣ በአረብነት…)፣ 3ኛ – የአገረ-መንግሥት ብሔርተኝነት (በአንድ አገር ዜግነት ላይ የተመሠረተ)፣ 4ኛ – የሃይማኖት ብሔርተኝነት (ለምሳሌ የእስልምና፣ የሂንዱ፣ የክርስትና…) እና 5ኛ – የአካባቢ ብሔርተኝነት ናቸው (ለምሳሌ የሸዋ፣ የሐረርጌ ብሔርተኝነት…)፡፡ በነዚህ የተለያዩ ብሔርተኝነቶች ውስጥ ግልጽ መሥመር የለም ስለዚህ አንዱ ከሌሎቹ በግልጽ አይለዩም፡፡ ከዚያም በላይ ሁሉንም ዓይነት ባሕሪ ያላቸው ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በኢትዮጵያ ግን በይበልጥ የሚታወቁት ሁለቱ ናቸው – የዘውጌ እና የኅብረት ብሔርተኝነት (pan-ethiopia nationalism፡ የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት)፡፡

ኢትዮጵያዊነትነት እንደዘር የሚቆጥሩት ብሔርተኞች አሉ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን እንደዜግነት ብቻ የሚቆጥሩት አሉ – ለነርሱ የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት የአገረ-መንግሥት ብሔርተኝነት ብለው ነው የሚቆጥሩት – በዜግነት ብቻ የሚገኝ ብሔርተኝነት አድርገው፡፡ ይህ ግን ለሌሎች ገና መዳረሻ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት የውጭ ጠላቶችን (ግብጽ፣ ቱርክ፣ ጣልያን፣ ሶማሊያ፣ ኤርትራ (ከተገነጠለች በኋላ)…) እና የውስጥ ጠላቶችን (የኤርትራ ብሔርተኝነት (ከመገንጠሏ በፊት)፣ የኦሮሞ ብሔርተኝነት፣ የኦጋዴን ብሔርተኝነት…) ማሰባሰቢያ መሣሪያ ያደርጋል፡፡ የዘውጌ ብሔርተኝነቶች ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔርተኝነትን እንደጠላት መዝግበው፣ እንደጨቋኝ ይታገሉታል፡፡ ምክንያቱም የአንዱ መጠንከር የሌላውን ያቀጭጫል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት ጎልቶ መውጣት፣ የዘውጌ ብሔርተኝነቶችን ያዳክማል፤ በተቃራኒውም የዘውጌ ብሔርተኝነቶች ጎልቶ መውጣት የኢትዮጵያ ብሔርተኝነቶችን ያዳክማል፡፡ ይህ በዐቃፊው እና ንዑስ ስብስቦቹ አማካይነት የተፈጠሩ ብሔርተኝነቶች መካከል የተፈጠረው ተቀናቃኝነት መንስዔው ዐቃፊው ብሔርተኛ መሠረቱን በዘውጌ ዓይን መመልከቱ ነው። የዘውጌ ብሔርተኞች የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት ንዑስ ስብስብ መሆን ሲገባቸወ፥ ፈፅሞ የማይቀላቀሉ (mutually exclusive) ናቸው የሚሉ አሉ።

በርግጥ የዘውጌ ብሔርተኞች እርስበርሳቸውም ይቀናቀናሉ፤ አንዳቸው ሌላኛቸውን በጠላትነት ይመድባሉ፡፡ ለምሳሌ የአማራ ብሔርተኞች እና የትግራይ ብሔርተኞች ዓይንና ናጫ ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር የኦሮሞ ብሔርተኞች ከሌሎች ዘውጌ ብሔርተኞች ጋር ያላቸው ቅራኔ ከኢትዮጵያ ብሔርተኞች ጋር ያላቸው ቅራኔ አይበልጥም፡፡   

‹ዘር› ወ ‹ዜግነት› ወ ‹ማንነት

‹ዘር› ለሚለው ቃል ብያኔ ለመፈለግ መሞከር በራሱ ‹ዘረኝነት› ነው ብለው የሚከራከሩ አሉ፡፡ ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ ከዚያም በታች ለመውረድ ስለሚቻል አያስፈራኝም፡፡ የአንድ ዘር ሰዎች በጥቅሉ የቆዳ ቀለም እና የፊት ቅርፅ ተመሳሳይነት ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያዊነትን እንደ ዘር የሚቆጥሩ ሰዎች የኢትዮጵያ ሶማሊ ከሶማሊ ሪፐብሊክ ሰዎች ጋር፣ የኢትዮጵያ ኑዌሮች ከሱዳን ኑዌሮች፣ የቦረና ኦሮሞዎች ከኬንያ ቦረናዎች፣ የኢትዮጵያ ትግራዋዮች ከኤርትራ ትግራዋዮች ጋር ልዩነት እንደሌላቸው ይዘነጉታል፡፡ ይህንን አልኩኝ እንጂ ሶማሊ ከአማራ ጋር ያለው ልዩነት ራሱ በዓይን የሚለይ አይደለም፡፡ የሆነ ሆኖ ዘር ሰፊ የሰዎች ስብስብ የያዘ ስለሆነ ከኢትዮጵያዊነትም ይሰፋል፡፡

በሌላ በኩል ማንነት ተቀራራቢ ምስስሎች ላይ ተመሥርቶ የሚሰጥ ድልድል ነው፡፡ በቋንቋ (ኦሮሞ፣ ሶማሊ…)፣ በመኖሪያ አካባቢ (ጎጃሜ፣ አዲስ አበቤ…)፣ በሃይማኖት (ሙስሊም፣ ክርስቲያን…)፣ በሙያ (መሐንዲስ፣ ጋዜጠኛ…)፣ እና ወዘተ. አንድ አገር ወይም ዘውግ የእነዚህ ሁሉ ቅይጥ ሊሆን ይችላል፡፡ ዜግነት የተሻለ አስታራቂ ይሆናል፡፡ ዜግነት በተለየ ድንበር ውስጥ የሚኖሩና በተለየ የሕግ ድንጋጌ የሚተዳደሩ ዜጎችን በሙሉ የሚያሰባስብ ማንነት ነው፡፡ ዜግነት ኢትዮጵያዊነትን ለመበየን ጤናማ መንገድ ነው፡፡  

‹ዘውጌ/ኅብረ-ብሔርተኝነት› ወ ‹የዜግነት ብሔርተኝነት›

ኢትዮጵያን እንደ አንድ ብሔር/ዘር የሚመለከቱ ሰዎች አሉ፡፡ እንደብሔር ስብስቦች የሚያዩ ሰዎችም አሉ፡፡ አሁን የሚበዙት እንደብሔር ስብስብ የሚመለከቷት ሰዎች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያን ኅብረ-ብሔራዊ ስብስብ አድርገው የሚመለከቱ ሰዎች የሚመለከቱበት ዓይን ዘውጌ ስለሆነ ኢትዮጵያዊነትን ለመግለጽ ሁሉም ባይቻልም፣ ብዙዎቹ የተሳተፉባቸውን ታሪካዊ ኩነቶች በማጉላት፣ ብዙዎቹን ቋንቋዎችንና ባሕሎችን በመዘርዘር ወዘተ ሲደክሙ ይስተዋላል፡፡ የኮታ ማሟላት እና በየኩነቱ ላይ ያንንም፣ ያቺንም ለመወከል ይፍጨረጨራሉ፤ መቼም ሙሉ ለሙሉ አይሳካላቸውም፡፡ ምክንያቱም አስተሳሰቡ ዘውጌ/ዘር ተኮር ነው፡፡ አመለካከቱ የብሔርተኝነት ነው፡፡

የዜግነት ብሔርተኝነት ከዚህ የተሻለ የሚሆነው ለዜጎች ሁሉ የዕኩል ዕድል እና ውክልና መንገዶችን በሕግ በመደንገግ እና ይህንን ሕጋዊ ድንጋጌ በማስከበር ይበየናል፡፡ በዋሽንግተን ዲሲ አማርኛ ቋንቋ አንዱ የሥራ ቋንቋ የሆነበት ምክንያት የዜግነት ብሔርተኝታቸው በሕግ የበላይነት ስለተከበረ ነው፡፡ የቋንቋ ልዩነት እና የውክልና ጉዳይ ገና አጀንዳ ከመሆኑ በፊት እንዲቀጭ የሚያደርግ የዕኩል ዕድል እና ውክልና መንገዶች ከተረጋገጡ ከላይ ያየናቸው ፈተናዎች አይመጡም፡፡

ልዩነቱን ለማሳየት ሪቻርድ ሒል የተባሉ የሚቺጋን ስቴት ዩንቨርስቲ ፕሮፌሰር የሁለቱን (የዘውግ እና የዜግነት ብሔርተኝነቶች) ልዩነት እንደሚከተለው ያስቀምጡታል፡- “የዘውግ ብሔርተኝነት መሠረቱ “ደም” ቆጠራ ነው፤ በደም የተቆጠሩት ሕዝቦች አገረ-መንግሥት ይኖራቸዋል፡፡ የዜግነት ብሔርተኝነት ግን መሠረቱ ሕጋዊ ዜግነት ነው፤ አገረ-መንግሥቱ ለዜጎቹ አገር ይሆንላቸዋል፡፡ […] ምንም እንኳን የወል ዘውግ መኖሩ የአንድን ዘውግ ሰዎች በሌሎች ላይ እንዲተባበሩ ቢረዳቸውም፣ ሌሎች የዘውግ፣ የመደብ፣ የሥርዓተ ፆታ፣ እና ሌሎችም ክፍፍሎች ላይ የተመሠረተውን ልዩነታቸውን እንዲያስታርቁ ሊረዳቸው ግን አይችልም፡፡ የዜግነት ብሔርተኝነት የሕግ እና ፖለቲካ ተሳትፎ ዕድሎችን በማመቻቸት ተፎካካሪ ቅሬታዎች/ፍላጎቶችን ለማመጣጠን ይረዳል፡፡ የዘውግ ብሔርተኝነትን ሊፎካከረው የሚችለው ብቸኛው አማራጭ ደግሞ የዜግነት ብሔርተኝነት ነው፡፡ ምክንያቱም የተለያዩ የዘውግ ቡድኖች ጎን ለጎን፣ በሠላም እና በመተማመን ሊኖሩ የሚችሉት ጠንካራ፣ ርትዓዊ እና ኢኮኖሚያዊ ውክልና ለሁሉም ማቅረብ የሚችል አገረ-መንግሥት ሲኖር ነው፡፡”

የብሔርተኞች ባሕርያት

ጆርጅ ኦርዌል ሦስት የብሔርተኛ ሰዎችን ፀባይ ለመለየት ሞክሯል፡፡ የአንድን ሰው ወይም ቡድን ብሔርተኛ ስሜት ለመገምገም በእነዚህ ሦስት ፀባዮች ብቻ መለካት በቂ ነው፡፡ 1ኛው – ሌላ ያለማሰብ አባዜ (obsession) ነው፡፡ ብሔርተኞች ከራሳቸው ቡድን የበላይነት ጉዳይ በቀር ሌላ ነገር ማሰብ አይችሉም፡፡ 2ኛው – በአንድ አቋም አለመፅናት (instablility) ነው፡፡ ብሔርተኞች ዛሬ የያዙት አቋም ነገ ላይኖር ይችላል፡፡ ታማኝነታቸው ለብሔርተኝነቱ እንጂ ለርዕዮተዓለሞች አይደለም፡፡ 3ኛው – ለሐቅ አለመጨነቅ (indifference to facts) ነው፡፡ በብሔርተኝነት ዓይን ድርጊቶች የሚገመገሙት ማን አደረጋቸው በሚለው እንጂ ምን ተደረገ በሚለው አይደለም፡፡

እነዚህ እና ከላይ ያየናቸው ነገሮች በሙሉ የሚያሳዩን ምንድን ነው? የብሔርተኝነትን ቅድስና ወይስ ርክሰት?

ቅድስና የጥቂቶች ነው!

ሰዎች ከራሳቸው ዕኩል ሌሎችን ሊወዱ ይችላሉ የሚለው እምብዛም አሳማኝ አይደለም፡፡ ሰዎች የሌሎችን ልጆች ከራሳቸው ልጆች ዕኩል የመቀበላቸው ነገርም እንደዚያው ነው፡፡ ሰዎች የሚከተሉትን እምነት ከሌሎች የተሻለ እና ምናልባትም እውነተኛ ነው ብለው ይገምታሉ፡፡ ብሔርተኝነትም እንደዚያው ነው፡፡ ሰዎች እነርሱ የተወለዱበትን ማኅበረሰብ፣ የሚከተሉትን እምነት እና አስተሳሰብ የሚያራምደውን ቡድን እንደትክክለኛ ሌላውን እንደተሳሳተ መቁጠራቸው የሚወልደው ነገር ነው – ብሔርተኝነት፡፡ ጥቂቶች ግን በዚህ ታጥረው አይቀሩም፡፡ የታሰሩበትን የውርስ ቅርፊት ሰባብረው ውጪውን ዓለም ለማየት የሚችሉ ጥቂቶች ይኖራሉ፡፡ ጥቂቶች እምነቴ የተሳሳተ ነው ብለው ሊቀይሩ የሚችሉትን ያክል ብሔርተኝነታቸውም የተሳሳተ እንደሆነ አምነው ወደ ሌላ ብሔርተኝነት የሚዘሉበት ዕድል አለ፡፡ ሁሉም እምነቶች ስህተት ናቸው ብለው ኢ-አማኒ የሚሆኑትን ያክል ሁሉም ብሔርተኝነቶች የተሳሳቱ ናቸው ብለው የሚያምኑበት ዕድል ይኖራል፡፡ ምናልባት ይህ ከብሔርተኝነት እርክሰት ወጥቶ ወደ ቅድስናው ምኩራብ መዳረሻ ይሆን ይሆናል፡፡ ችግሩ ‹ብዙኃን እዚህ ምኩራብ የሚደርሱት መቼ ነው?› የሚለው ነው፡፡ ምክንያቱም ‹ብዙኃን ይመውዑ› ይባላል – ትክክል ቢሆኑም ባይሆኑም ብዙኃን ይፈርዳሉ፡፡

ነገሮችን አቃልሎ እና ሸንሽኖ ለመረዳት መሞከር ጠቃሚ የሚሆንበት አጋጣሚ ቢኖርም፥ ሁሌም ትክክለኛ ውጤት አያስገኝም። አገርን የሚያክል ትልቅ ፅንሰ-ሐሳብ በግለሰብ ርስት ዓይን  ለመረዳት መሞከርም ከዚህ ዓይነቱ አደገኛ ስህተቶች አንዱ ነው። በኢትዮጵያ ‘እከሌ የተባለው ግዛት የማን ነው?’ እና ‘እከሌ የተባለውን ግዛት ማን ያስተዳድር?’ የሚሉት ጥያቄዎች ዐውድ በጣም አሳፋሪ እና ‘ገና በዚህ ጉዳይ እንኳ መግባባት አልቻልንም እንዴ?’ በሚል ራሳችንን እንድንታዘብ የሚያደርግ የዘወትር ገጠመኝ ነው። 
‘አዲስ አበባ የማነች?’ የሚለውን ጥያቄ ደጋግሞ መስማት አስደናቂ አይደለም። የቡድን ሥም እየጠሩ፣ ታሪክ እየደረደሩ የባለቤትነት ማስረጃ ለማምጣት የሚሞክሩትን ሰዎች መከራከሪያ ማድመጥም የከተማዋን ኅልውና ያክል አዲስ ነገር አይደለም። የዚህ ጽሑፍ መነሻም የምክትል ከንቲባዋን ሹመት ተከትሎ የዚህ ክርክር እንዳዲስ ማገርሸት ነው። አዲስ አበባ የማን ነች? እነማን ናቸው ሊያስተዳድሯት የሚገባቸው? መጀመሪያ ግን ኢትዮጵያ ራሷስ የማነች?
ኢትዮጵያ የማነች?
ቢያንስ ለዚህ ጽሑፍ ሲባል ኢትዮጵያ የምንላት ሕዝቧን፣ ግዛቷን፣ መንግሥቷን እና ሌሎች የዓለም መንግሥታት የሚቀበሉትን ሉዓላዊነቷን ነው። ሉዓላዊነት የአገር ፅንሰ-ሐሳብነት መገለጫ ነው። በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ላይ የኢትዮጵያ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤቶች “የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች” ናቸው (አንቀፅ 8)። ይህ ማለት ‘ኢትዮጵያ የኦሮሞ፣ አማራ፣ ሶማሌ፣ ትግራዋይ፣ ወዘተ የጋራ ንብረት ናት’ የሚል ትርጉም ይሰጣል። ከላይ ሲታይ ‘ኢትዮጵያ የሁሉም ናት’ የሚል ጭብጥ ያለው ይመስላል። ነገር ግን በዚህ ብያኔ እያንዳንዱ ዜጋ የኢትዮጵያ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለድርሻ መሆን አይችልም። ‘የኢትዮጵያ’ የሚባሉት ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች አባል ያልሆነ የኢትዮጵያ ዜጋ የሉዓላዊ ሥልጣኑ ባለቤት መሆን አይችልም።
ነገሩን በቀላል ምሳሌ ለማስረዳት ያክል፥ ሕገ መንግሥቱ “የውጭ አገር ዜጎች የኢትዮጵያ ዜግነት ሊያገኙ ይችላሉ” ይላል(አንቀፅ 6)። እነዚህ የኢትዮጵያ ዜግነት የተሰጣቸው የሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤት ናቸው ወይስ አይደሉም? ባለቤት እንዲሆኑ አንዱ የኢትዮጵያ ብሔረሰብ አባል ሆነው ዜግነት መቀበል አለባቸው ማለት ነው። ይህ ደግሞ አያስኬድም፤ ምክንያቱም ሰዎች የኢትዮጵያ ዜግነትን ለመቀበል፥ የራሳቸውን የዘውግ ማንነት እንዲክዱ እና አዲስ እንዲቀበሉ ማስገደድ አይቻልም። በጥቅሉ ይህ ድክመቱ የኢትዮጵያን ሕገ መንግሥት ዜጎች ሁሉ የአገር ሉዓላዊ ባለቤትነት ዕኩል ድርሻ የሌላቸው በማድረግ አስገራሚ ገጽታ ያላብሰዋል። ይህ ችግር የተከሰተው ኢትዮጵያዊ ዜግነት የተመሠረተው በዜግነት መብቶች ሳይሆን በቡድን ማንነት መብቶች በመሆኑ ነው። ለዚህ ነው በዜግነት-ብሔርተኝነት (civic nationalism) የሚመራ ‘ኢትዮጵያዊነት’ መመሥረት ያልተቻለው። የሁሉም የተባለ ነገር የእያንዳንዱ የመሆን ዕድሉ አናሳ ነው። የእያንዳንዱ የሆነ ነገር ግን የሁሉም መሆን ይችላል። 
‘ኢትዮጵያ የማናት?’ የሚለው ጥያቄ ‘የእንዳንዱ/ዷ ዜጎቿ’ የሚል መልስ እስከሚያገኝ ድረስ፥ የክልሎች፣ የክፍለ ክልሎች የማንነት ጥያቄም እንዲሁ አጥጋቢ መልስ አያገኝም። ምክንያቱም የአስተሳሰብ ናሙናው አንድ ዓይነት ነው። ችግሩ አንድ አገር ባለቤት ለመሆን የሚገባቸው እና የሚመጥኑ ጥቂት የማሕበረሰብ ክፍሎች ብቻ ናቸው ብሎ ከማሰብ የሚመነጭ ነው። በርግጥ አገራት የተገነቡት በረዥም የፖለቲካ ሒደት፣ በፍጭት እና ማመቻመች ነው። ይሁን እንጂ በተለይ በዚህ ትውልድ ላይ የሚገኙ ሰዎች አገሮቻቸውን በምርጫ አላገኙም፥ በአገረ መንግሥት ግንባታው ላይም አልተሳተፉም (እንደኤርትራ ያሉትን አዳዲስ አገራት ለጊዜው እንዘንጋቸው)። እናም በዓለም የተከፋፈሉት ድንበሮች ለሠላም እና ስርዓት (order) ሲባል ዕውቅና ተሰጥቷቸው ይኖራሉ እንጂ የአንድ አገር ዜግነት ለመሆን ዘር አይመረጥም፤ ይህ በየትኛውም ዓለም ዐቀፍ ሕግ ተቀባይነት የለውም። በሕግ አግባብ ዜጋ የሆኑ ሁሉ ደግሞ የአገር ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤቶች ናቸው። ይህ በኢትዮጵያ አልተከበረም፤ በሕግም፣ በአስተሳሰብም። ስለዚህ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ በተከፋፈሉት አስተዳደራዊ ክልሎች እና ክልላዊ ሕገ መንግሥታትም ተመሳሳይ ችግሮች ይስተዋላሉ። 
የክልል ሕገ መንግሥታት የክልሉ ‘መሥራቾች’ እና ‘ባለቤቶች’ የሚሏቸው ፅንሰ-ሐሳቦች አሏቸው። በሚያሳዝን ሁኔታ፣ ክልሎቹ ሲመሠረቱ እና ፌዴራል ስርዓቱ ሲዘረጋ ነዋሪ የነበሩ ዜጎች ሳይቀሩ የክልሎቹ ‘መሥራቾች’ ተብለው ባለመቆጠራቸው ምክንያት የዜግነት መብቶቻቸው እንኳን አልተከበሩላቸውም። ይልቁንም ‘መጤ’ በሚል ቃል እና ‘እንግዳ’ በሚል መጠሪያ ማሸማቀቅ እና ማሳደድ እንደሞያ ተይዟል። በየቦታው በርስት እና የተፈጥሮ ሀብት ግጭት የበረከተው ግጭት፣ ዜጎችን በሕጋዊ መንገድ ከሚኖሩበት ቀዬ የማፈናቀል ደዌ የተባባሰው፥ በከፊል ዜጎች የባለቤትነት ስሜት እና በከፊሎቹ የባይተዋርነት ስሜት ነው። አገርን ወይም ክፍለ አገርን የተወሰኑ ዜጎች ርስት አድርጎ የመቁጠር አባዜ ነው፥ እኔ ከእከሌ የበለጠ ባለቤት ነኝ የሚለው አስተሳሰብ በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት እና በየክልሉ ሕገ መንግሥታት እንዲሁም በየግለሰቡ አእምሮ ውስጥ ተዘርቶ የበቀለው። 
አዲስ አበባን እነማን ያስተዳድሯት? 
አዲሱን የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (በሙሉ የከንቲባ ሥልጣን) መሾም ተከትሎ የአዲስ አበባ ባለቤት እና አስተዳዳሪ ጉዳይ የተለመደ ሙግት አገርሽቷል። በሚያሳዝን ሁኔታ ከጥቂት የሕጋዊ አግባብነት እና የቅቡልነት ጥያቄ ካነሱት ተቺዎች በስተቀር፥ ሹመቱን የተቃወሙትም ይሁኑ የደገፉት ከላይ በተጠቀሰው የአስተሳሰብ ደዌ ተነድተው ነው ማለት ይቻላል። በተለይም ደግሞ ምክትል ከንቲባው ‘ኦሮሞ ስለሆኑ ይገባቸዋል’ እና ‘ኦሮሞ ስለሆኑ አይገባቸውም’ የሚሉት ሁለቱም አንድ ዓይነት ስህተት ሠርተዋል። 
በዚህ በኩል የአዲስ አበባን ነዋሪዎች ቁጥር በብሔር ሸንሽነው ‘አማራዎች ብዙ ነን፤ መምራት ያለብንም እኛው ነን’ ይላሉ። በወዲያ በኩል ደግሞ ‘የታሪክ ባለቤትነቱ የኦሮሞ ስለሆነ አስተዳደሩ የእኛ መሆን አለበት’ ይላሉ። እንደገና በዚያ በኩል ደግሞ ‘በታሪክ ከተባለማ ወደኋላ በተጓዝን ቁጥር የእኛ ነበር’ ይላሉ። በወዲያ በኩል ደግሞ ‘በሕገ መንግሥቱ እና በጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ የእኛ ባለቤትነት ተረጋግጧል’ የሚል ክርክር ይመጣል። በዚህ ብቻ አይወሰንም፤ ‘አዲስ አበባ ተወልደው ባደጉ ‘ልጆቿ’ መመራት አለበት’ የሚሉ አሉ። በባለቤትነት እና በአስተዳዳሪነት ይገባኛል ሽሚያ ውስጥ ሙያዊ ብቃት፣ የነዋሪው ምርጫ እና ይሁንታ ከቁብ አልተጻፈም፤ ብቸኛው ቁምነገር መወለድ ብቻ ይመስላል።
‘አዲስ አበባን እነማን ያስተዳድሯት?’ በሚለው ጥያቄ ውስጥ ቁም ነገሩ መወለድ ብቻ ተደርጎ መታሰብ ካልቀረ በቀር፥ የአዲስ አበባ ባለቤትነት ጥያቄም ማጨቃጨቁ አይቆምም። አዲስ አበባን የአዲስ አበባ ነዋሪ እስከሆኑ፣ የነዋሪዎቿን ቅቡልነት ባገኘ ምርጫ እስከተመረጡ ድረስ የቻይና ዘር ያለው የኢትዮጵያ ዜጋም ቢሆን፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ ወይም ሱማሊ ክልል ተወልዳ ያደገችና በኋላ የአዲስ አበባ ነዋሪም የሆነችም ብትሆን መምራት ትችላለች። በመወለድ የሚገኝ የማስተዳደር መብት የለም። እንዲህ ከሆነ የአዲስ አበባ ግዜያዊ ባለቤቶች በወቅቱ ነዋሪዎቿ ይሆናሉ። 
‘ልዩ ጥቅም’ vs. ‘ባለቤትነት’
የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 49/5 «የኦሮምያ ክልል፤ የአገልግሎት አቅርቦት ወይም የተፈጥሮ ሀብትን አጠቃቀምንና የመሳሰሉት ጉዳዮችን በተመለከተ እንዲሁም አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሐል የሚገኝ በመሆኑ የሚነሱ ሁለቱን የሚያስተሳስሩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ያለው ልዩ ጥቅም ይጠበቅለታል» ይላል። ይህንን በተሳሳተ መንገድ የሚረዱት ብዙ ናቸው። 
ልዩ ጥቅሙ አዲስ አበባ በአንድ በኩል የመጠጥ ውኃ እና ሌሎችም ከአጎራባቿ የኦሮምያ ክልል አስተዳደራዊ አካባቢዎች የምታገኝ በመሆኑ፤ በሌላ በኩል ቆሻሻዎቿን የምታራግፍበት እና የበከለችውን ወንዝ የምታስወግድበት እና ሌሎችንም ጫናዎች የምታሳድርበት በመሆኑ ለጥቅሟና ጉዳቷ እንደክፍያ የሚሰጥ ጥቅም ነው እንጂ የልዩ ባለቤትነት ዐዋጅ አይደለም። ይህ ጉዳይ አዲስ አበባ የየትኛውም ክልላዊ አስተዳደር መሐል ብትገኝ ኖሮ ማድረግ የሚገባት ጉዳይ ነው። በርግጥ ልዩ ተጠቃሚዎቹ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉት አካባቢዎች ናቸው መሆን የሚኖርባቸው። የሆነ ሆኖ ያ የሚደረገው በክልሉ አማካይነት ነው። ነገር ግን ኦሮምያ የኢትዮጵያ አካል መሆኗ ቀርቶ ነፃ መንግሥት ብትሆን እንኳን የአዲስ አበባ ጊዜያዊ ባለቤቶች ነዋሪዎቿ፣ አስተዳደሮቿም የነዋሪዎቿ ምርጫዎች ናቸው የሚሆኑት። ከዚያ ውጪ ያለው ሁሉ ሕጋዊ ቅቡልነት የለውም። በሕግ ቢደነገግም ፍትሐዊ ስለማይሆን ተቀባይነት አይኖረውም።

አሁን ያለንበት ሁኔታ “ታስሮ የተፈታ ጥጃ” ሁኔታ ነው። መዝለል እና መቦረቅ – የነፃነታችንን ልክ መፈተን የምንፈልግበት ወቅት ነው። ምክንያቱም ነፃነታችን ከእስር የተፈታው ገና አሁን ነው፣ የዴሞክራሲ ባሕል አልነበረንም፣ በዚያ ላይ ያልተመለሱ እልፍ ጥያቄዎች አሉን። ይሁን እንጂ ሲደክመን እንሰክናለን። መዝለል ስለምንችል ብቻ አንዘልም። መርገጥ ስለምንችል ብቻ አንራገጥም። ያልተመለሱ ጥያቄዎችን በተደራጀ፣ በሕጋዊ እና ሠላማዊ መንገድ ታግለን ማስመለስ እንጀምራለን። ከዚያ በፊት ግን ዝላያችን እና እርግጫችን ለገዢዎቻችን የለውጡን ተስፋ ለመቀልበሻ፣ እኛን መልሶ ለመርገጫ ምክንያት እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል።
አንዲት ኤርትሪያዊት የትዊተር ተጠቃሚ፣ ‘ሰውያችሁ ባለ ግርማ ሞገስ እና ጥሩ ተናጋሪ በመሆኑ እንዳትሸወዱ፣ የእኛም መሪ እንደዛ በመሆኑ የለውጡን ተቋማዊነትን ሳናረጋግጥ ነው ለዚህ የተዳረግነው’ የሚል መልዕክት ለኢትዮጵያውያን አቻዎቿ አስተላልፋለች። አዎ፣ የዛሬው ታላቁ አምባገነን ኢሳያስ አፈወርቂ፣ የዛሬ 27 ዓመት ገደማ በኤርትራውያን ዘንድ ታላቅ ሕዝባዊ ይሁንታ ያለው መሪ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከራሳቸው መጠበቅ” በሚለው ጽሑፌ ‘ብዙዎቹ ነጻ አውጪዎች ኋላ አምባገነን ይሆናሉ’ ማለቴን እንደ ጅምላ ድምዳሜ የወሰዱብኝ አስተያየት ሰጪዎች አሉ። እኔ ለማመልከት የፈለግኩት በአንድ ወቅት ‘ነጻ አውጪ’ የነበረ፣ ሌላ ግዜ ‘አምባገነን’ እንደማይሆን አያረጋግጥም ነው። ይህ እንዳይሆን ብቸኛው ዋስትና ‘ቁጥጥርና ሚዛን’ (check and balance) ነው። ትላንት ጓደኞቼ ስለ ኢዲ አሚን ዳዳ አንድ ጽሑፍ እያስነበቡኝ ነበር። ከዓለማችን የምንግዜም አምባገነኖች አንዱ የሆነው ኢዲ አሚን በሥልጣን አፍላው ዘመን በምዕራባውያን ሚዲያዎች ሳይቀር የተንቆለጳጰሰ ሰው ነበር። ሰውን አምባገነን የሚያደርገው ተቋማዊ ነጻነት አለመኖሩ እና የግለሰቦች ሥልጣን አለመገደቡ ነው። 
ኢትዮጵያ ለውጥ ለምን አይዋጣላትም?
ይህንን ጥያቄ ያነሳሁት አሁን ያለንበትን የለውጥ ተስፋ ጥላሸት ለመቀባት ወይም ተቀልብሷል ለማለት አይደለም። ለውጡ ከግለሰቦች በጎ ፈቃድ ወደ ተቋማዊ እውነታነት እንዲሸጋገር ካለኝ ጥልቅ ጉጉት ነው። ሁሉም ሰው የለውጡን አካሔድ በጥንቃቄ እንዲመለከተው ስለምፈልግ ነው።
ኢትዮጵያ እንዲህ የለውጥ ተስፋ ውስጥ የገባችው አሁን ብቻ አይደለም። የንጉሣዊው ስርዓት መደርመስ እና የመሬት ላራሹ መታወጅም ግዙፍ ሕዝባዊ ይሁንታ እና ተስፋ ፈንጥቆ ነበር። የምርጫ 1997 ዋዜማ አገራችን የመጀመሪያውን ዴሞክራሲያዊ ለውጥ ልታካሒድ ነው በሚል ትልቅ ተስፋ
ፈንጥቆ ነበር። ሌላው ቀርቶ የደርግ መውደቅ እና በሌላ ታጣቂ መተካት ትልቅ የለውጥ ተስፋ ፈንጥቆ ነበር።
ከ’ያ ትውልድ’ ሰዎች አንዱ ገጣሚ ኃይሉ ገ/ዮሐንስ (ገሞራው) ‘ኢትዮጵያ ለውጥ የማይዋጣላት አበውን አጠያይቄ በነገሩኝ መሠረት “ተረግማ ነው”‘ በሚል በ1993 ‘ኢትዮጵ’ መጽሔት ላይ ተከራክሯል። ዐፄ ቴዎድሮስ ራሳቸውን ሲያጠፉ፣ ዐፄ ዮሐንስ በደርቡሾች አንገታቸው ሲቀላ፣ ልጅ እያሱ ሲገደሉ፣ አቡነ ጴጥሮስ በጣሊያን ሲረሸኑ፣ ደጃች በላይ ዘለቀ እና ጄነራል መንግሥቱ ነዋይ በአደባባይ ሲሰቀሉ፣ ዐፄ ኃይለሥላሴ ሲገደሉ በአገራቸው አዝነው እና ተማርረው ነው በሚል ገሞራው ተከራክሯል።
እኔ ግን በእርግማን አላምንም። እንመን ቢባል እንኳ በጥቂቶች ጥፋት ብዙዎች የሚቀጡበት ምክንያትም አይኖርም። ለውጥ የማይዋጣልን ለቅድመ ለውጡ የምንከፍለውን መስዋዕትነት ሩቡን እንኳን ለውጡን ለማስጠበቅ ስለማንከፍል ነው። ከዚያም በላይ የከፋው ደግሞ ተረኛ ጨቋኝ እንመርጣለን እንጂ ነፃነትን ብቻ ዒላማ አድርገን ስለማንመርጥ ነው። ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ደግመው ደጋግመው እንደተናገሩት ‘ኢትዮጵያውያን ተጨቋኝነትን እንጂ ጭቆናን አንቃወምም’።
ሁለቱ ፅንፎች
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ያለፉትን ሦስት ስርዓቶች ተቃውመዋል በሚል ነው ሥማቸው የሚነሳው። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይን መምጣት በሙሉ ይሁንታ ከተቀበሉ ሰዎች ሁሉ የእርሳቸውን አስገራሚ የሚያደርገው የተቃዋሚነታቸው ታሪክ ነው። እንደ እርሳቸው ከሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይን ወደ ሥልጣን ያመጣቸው ‘ኢትዮጵያ የተአምር አገር መሆኗ ነው፤ እግዚአብሔር ኢትዮጵያን እንደማይታዋት ማሳያ ነው’።
በሌላ በኩል፣ ከኢንሳ ኃላፊነታቸው የተነሱት ጄኔራል ተክለብርሃን በትግራይ ቲቪ ቀርበው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ትሕነግን (TPLF) ለማጥፋት ያለሙ ሰው እንደሆኑ አድርገው ገልጠዋቸዋል።  ‘አካሔዳቸው ፕሬዝደንታዊ ዓይነት ነው። ሕግ ይጥሳሉ፣ እስረኛ ይፈታሉ፣ አሸባሪ ይጠራሉ፣ ባድመን ሕግ ተላልፈው ያለ ቅድመ ሁኔታ ሰጥተዋል፣… እየተመራን ያለነው በጁንታ ነው’ ብለዋል።
ፕሮፌሰር መስፍን የኢትዮጵያ አንድነት ከምንም በላይ የሚያሳስባቸው ሰው ናቸው። የድጋፋቸው እና የደስታቸው ምንጭም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አመጣጥ ኢትዮጵያ ካሁን አሁን ወደ ቀውስ ገባች እየተባለ ባለበት በኢትዮጵያ ሥም እየማሉ የሚገዘቱ መሪ ሁነው፣ አመፁን ሁሉ ፀጥ ማስባል በመቻላቸው ነው። በተቃራኒው የትሕነግ ሰዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩን እና ተቀባይነት ያስገኘላቸውን ለውጥ የሚቃወሙት ቀድሞ የነበራቸውን የበላይነት ስለሚቀማቸው ነው። የበላይ ፈላጭ ቆራጭ ለነበረ ሰው ዕኩልነት አዋጭ አይደለም። የለውጡ ድባብ ግን ከነዚህ ዕኩልነት አያዋጣንም ከሚሉት ውጪ ያሉትን ከሞላ ጎደል አስማሚ ነው። ለአገር ተቆርቋሪ የሆኑትን ከመፍታትም በላይ፣ ተሰደው የከረሙትንም ወደ አገር ቤት የሚመልስ የለውጥ ድባብ ነው ያለው። 
ቀጣዩ ግጭት የሚነሳው በሁለቱ ፅንፎች መካከል ነው ብዬ እሰጋለሁ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚመሩት የለውጥ መንፈስ ደጋፊዎች እና የለውጥ መንፈሱን በሚቃወሙት መካከል። የለውጡ መንፈስ ደጋፊዎች ብዙኃን ቢሆኑም በኢኮኖሚ እና በመዋቅር አልተደራጁም። የለውጡ መንፈስ ተቃዋሚዎች የድርጅት መዋቅሩ ብቻ ሳይሆን ኢኮኖሚያዊ አቅሙም አላቸው። ለዚህም ይመስላል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በገደምዳሜም ቢሆን ‘ለውጡን ጠብቁ’ የሚል መልዕክት የሚያስተላልፉት። በርግጥ ትሕነግም በመግለጫ ሳይቀር ተቃራኒው እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል። ለውጡን ጠብቁ የሚለው ጥሪ እና ዛቻ ብዙ አብዮቶች እንዲቀለበሱ ሰበብ የሚሰጣቸው “ፀረ አብዮቶችን የመመንጠር ዘመቻ” ጋር ስለሚመሳሰልብኝ ያስደነግጠኛል። ይሁን እንጂ የሚከተለውን ጥያቄ አቀርባለው። 
የትኛውን ለውጥ እንጠብቅ?
እስረኞችን የመፍታት እርምጃው ለውጥ ነው። ይሁን እንጂ ድርጊቱ የተፈፀመው በሕጋዊ አግባብ ሳይሆን በፖለቲካ አመራሮቹ መልካም ፈቃድ ነው። (እርግጥ አሁን ዐዋጁም እየተሻሻለ ስለሆነ በአስቸኳይ መፍትሔ የተስተካከለው በሕግ እየፀና ነው እና ትክክለኛ አካሔድ ነው። ይህንን ግን በሁሉም ረገድ እንዲቀጥል ማድረግ ነው ‘ለውጡን መጠበቅ’ ማለት ሊሆን የሚችለው።) በሕግ ያልተፈቀዱ ባንዲራዎች ያለምንም ስጋት አደባባይ ላይ እንዲውለበለቡ ተፈቅዷል። በእርግጥ ሕጎቹ ፍትሓዊ ባለመሆናቸው ድርጊቱ/ለውጡ መልካም ነው። ነገር ግን በፖለቲካ አመራሮቹ ይሁንታ ብቻ የተደረገ ስለሆነ ሕጋዊ ዋስትና የለውም። የባንዲራን ጉዳይ እንደምሳሌ አነሳሁት እንጂ በሁሉም እርምጃ አካሔዱን ማስተዋል እና መገምገም አለብን። 
የፖለቲካ መሪዎች የመፍቀድ መብት ካላቸው፣ የመከልከልም ይኖራቸዋል። የፖለቲካ መሪዎች ሥልጣን ተለጥጦ በጎ ፈቃዳቸው ለብዙኃኑ ተስማሚ እስከሆነ ድረስ ችግሩ አይስተዋልም። ችግሩ ይህንኑ ሥልጣናቸውን ለብዙኃኑ ተስማሚ ባልሆነ መንገድ የተጠቀሙበት ግዜ ነው የሚመጣው። በርግጥ ቅንነት ከፖለቲካ ምኅዳራችን የተሰወረ ነገር በመሆኑ አሁን መከሰቱ ግሩም ነው። ነገር ግን የብዙኃኑ ተጠቃሚነት በጥቂት ባለሥልጣናት ቅንነት እና በጎ ፈቃድ ላይ ተንጠልጥሎ መቀመጥ የለበትም። ምክንያቱም ደግሞ ባለሥልጣናቱ ዘላለም የማይኖሩ ከመሆኑም ባሻገር ቅንነታቸውም ዘላለም ላይኖር ይችላል።
መፍትሔው የተለያዩ ተቋማት ነጻ እና ገለልተኛ እንዲሆኑ አድርጎ መገንባት ነው። መወገን ካለባቸውም ለሕዝብ እና ሕገ መንግሥቱ መሆን አለበት። ለውጡን ስንደግፍ የምናየው ለውጥ ሕጋዊ ዋስትና እንዲኖረው፣ ተቋማዊ ነጻነት እንዲጠናከር፣ የፍትሓዊ ሕግ የበላይነት እንዲስፋፋ ግፊት በማድረግ መሆን አለበት። አለበለዚያ ይህም ዕድል ያመልጠናልና ብዙ መስዋዕትነት የተከፈለለትን ለውጥ በዚህ መንገድ እንጠብቅ። 

ከእኛ አገር የማያልቁ ችግሮች መካከል አንዱ የማንነት አረዳድ እና አበያየን ጉዳይ ነው። ማንነት እና ምንነት የፖለቲካ ጫወታችን አስኳል ሆኖ ሳለ፣ የማንነት አበያየናችን ግን ግለሰቦች የራሳቸውን ማንነት የሚበይኑበት ነጻ ዕድል የማይሰጥ ነው። 
የኦነጉ በያን አሶባ ባንድ ወቅት ከኢሳት ቴሌቪዥን “ኦሮሞ ማነው?” የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር። “ኦሮሞ ነኝ ያለ” የሚል ምርጥ መልስ ሰጥተዋል። ነገር ግን ብዙዎች ማንነትን በዘር የሚወረስ እንጂ በማኅበራዊ-ሥሪት (social construction) የሚመጣ ነገር አድርገው አይመለከቱትም። እውነት መሆኑን ከራሷ ማረጋገጥ አልቻልኩም እንጂ ድምፃዊ ሴና ሰለሞን ከአማራ ተወላጆች የተወለደች ኦሮሞ ነች፤ “ኦሮሞ ነኝ” ስላለች። ራሷን የምትገልጸው እንደ ኦሮሞ ሲሆን፣ በዘፈኖቿ የታገለችውም ለኦሮሞ ሕዝብ ነጻነት ነው። የወላጆቿ የማንነት ታሪክ የሐሰት ወሬ ቢሆን እንኳ ነባራዊ ምሳሌ እናጣለን እንጂ፣ ምሳሌው ማንነትን የመምረጥ ግለሰባዊ ነጻነቱን የተሳሳተ አያደርገውም። 
‘ኢትዮጵያዊ ማንነት አለ፣ የለም? ጎጃሜ ማንነት አለ፣ የለም? አዲሳበቤ ማንነት አለ፣ የለም?’ የሚሉት ጉንጭ አልፋ ክርክሮች ምንጫቸው የግለሰቦች ማንነት እኛ ራሳችንን እንዲሁም ሌሎችን ከምንረዳበት መንገድ ውጪ መወሰን የለበትም ከሚል አስተሳሰብ የመነጨ ነው። በቀላል ቋንቋ ለመግለጽ አባባሉ “እኔ ናችሁ ከምላችሁ ውጪ መሆን አትችሉም” ነው። 
በበኩሌ ሰዎች የራሳቸውን ማንነት ብለው የሚጠሩት ወይ ‘የሚኮሩበትን’ አሊያም ‘የተበደለባቸውን’ [ወይም የተበደለባቸው የሚመስላቸውን] ማንነታቸውን ነው ብዬ ነው የማምነው። ይሁን እንጂ ሁሉም ሰዎች ማኅበራዊ ሥሪታቸው ከብዙ ድርብ፣ ድርብርብ ማንነቶች የተገነባ ነው። ጥቁር ሕዝብ መሐል ላደጉ ኢትዮጵያውያን ጥቁርነት የማንነታቸው መገለጫ መሆኑ ትዝ ብሏቸው አያውቅም። ነገር ግን ከኢትዮጵያዊ ወላጆች ተወልደው ነጮች አገር ያደጉ ኢትዮጵያውያን “ምንድን ነህ/ምንድን ነሽ?” የሚል ጥያቄ ቢቀርብላቸው፣ ጥቁርነታቸው ቀድሞ የሚመጣባቸው መልስ ሊሆን ይችላል? “ምንድን ነህ/ነሽ?” የሚለው ጥያቄ የማንነት ወይም የምንነት ጥያቄ መሆኑ አያጠራጥርም። መልሱ ግን ወጥ አይደለም። እንደ ሁኔታው እና ቦታው ይለያያል። አንዱ “አካውንታንት ነኝ” ብሎ ሙያውን እንደማንነቱ መገለጫ ሊጠቅስ ይችላል፣ ሌላዋ “ሙስሊም ነኝ” ልትል ትችላለች። በሁኔታው፣ በወቅቱ እና በቦታው ሰዎች ስለማንነታቸው የሚሰማቸው ስሜት የተለያየ ሊሆን ይችላል። ይህም የማንነትን ወጥ አለመሆንና ድርብርብነት ያረጋግጣል።
እኔ በማንነቴ ቀረፃ ውስጥ “የድሀ ልጅ” መሆኔን ያክል ተፅዕኖ የፈጠረብኝ ነገር አለ ብዬ አላምንም። የድሀ ልጅ ሆኖ ማደግ ያለንን ነገር ‘ላጣው እችላለሁ’ በሚል ፍርሐት እና የሌለንን ነገር ‘ላገኘው አልችልም’ በሚል ስጋት ውስጥ መኖር ማለት ነው። ይህ ማንነት ነው። በድህነት ውስጥ ላደገ ሰው፣ ዓለም ማለት የመግዛት አቅም ባላቸው እና በሌላቸው ሰዎች የተሞላች ናት። የአዲስ አበባ ድሀ፣ ከብራዚል ድሀ ጋር በሥነ ልቦና የሚያግባባ ማንነት አለው። ነገር ግን “የድሀ ልጅ” የሚባል ማንነት በኛ የፖለቲካ መዝገበ ቃላት የለም። ስለዚህ ከዚህ ውጪ ብዙ ማንነቶች አሉኝ። ለምሳሌ ጦማሪነት። ከዚህ በፊት ስታሰር ስፈታ የነበርኩት ተቺ ጦማሪ ስለሆንኩ ነው። ስለዚህ ምንድን ነህ ስባል ‘ብሎገር ነኝ’ የምልባቸው ግዜያት ብዙ ናቸው። ለምሳሌ እስር ቤት በማንነቴ ነው የታሰርኩት የሚሉ ነበሩ። እነሱ “ኦሮሞ በመሆኔ”፣ “አማራ በመሆኔ” ሲሉ እኔ ደግሞ “ብሎገር በመሆኔ” እል ነበር። ይህም ማንነት ነው። ይህንን ብነፈግ እንኳ በትምህርት ያፈራሁት፣ በተወለድኩበት አካባቢ ያፈራሁት፣ በእምነቴ ወይም ባለማመኔ ያፈራሁት ብዙ ማንነቶች አለኝ። 
ነገር ግን በኢትዮጵያ ፖለቲካ ብያኔ መሠረት እነዚህ ሁሉ ማንነቶቼ ዋጋ የላቸውም። “ምንድን ነህ?” ስባል የወላጆቼን የዘውግ ማንነት እንድናገር ይጠበቅብኛል። ወላጆቼ ቅይጥ ቢሆኑ እንኳን የአባቴን [ይህ ካልሆነ ደግሞ የእናቴን] የዘውግ ቡድን ማንነቴ ብዬ እንድናገር ይጠበቅብኛል። እኔ እኔን ይገልጸኛል የምለው ማንነት እንዲኖረኝ ነጻነቱ የለኝም። በዚህ አካሔድ “ኦሮሞ ነኝ” ማለት፣ ወይም “አማራ ነኝ” ማለት፣ ወይም “አዲሳበቤ ነኝ” ማለት ምንም ዋጋ/ጥቅም የለውም። ምክንያቱም በኔ ማንነት ላይ እኔ የመወሰን ነጻነቱ የለኝም። 

ፎቶው ላይ ከግራ ወደቀኝ የሚታዩት፤ የኮንሶ መሪ ካላ ገዛኸኝ እና ወንድማቸው
በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ሕዝባዊ አመፆች በተቀጣጠሉበት ወቅት፣ በሕዝብ ብዛት ትንሿ ኮንሶም ከዐሥር ወራት ላላነሰ ጊዜ ሕዝባዊ ተቃውሞ ታደርግ ነበር። በወቅቱ የመብት ተሟጋቾች አመፁ አገር ዐቀፍ እንደሆነ ለማስረዳት እንደምሳሌ የኮንሶን ጉዳይ ደጋግመው ይጠቅሱት ነበር። በወቅቱ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሠላማዊ ተቃውሞዎችን በኃይል በመበተን፣ ብዙዎችን ወደ እስር ቤት አጉረዋል። ከነዚህ እስረኞች ውስጥ የኮንሶ የጎሳ መሪ የሆኑት ካላ ገዛኸኝ ወልደዳዊት ካዮቴ ይገኙበታል። (‘ካላ’ በጎሳ መሪነት የሚገኝ የጎሳ ሐረግ ማዕረግ ነው።)
ካላ ገዛኸኝ ከመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ በሲቪል ምሕንድስና ተመርቀዋል። የጎሳ መሪነቱን ከአባታቸው የወረሱት በጥቅምት 2006 በባሕላዊው ወግ መሠረት ከአባታቸው ነበር። የጎሳ መሪው በኮንሶ ማኅበረሰብ ልማድ መሠረት ልማዳዊ ዳኝነት፣ ግልግል እና ሌሎችም ማኅበራዊ አስተዳደር ይሰጣል። ይሁን እንጂ የአሁኑ የጎሳ መሪ ካላ ገዛኸኝ ሠላማዊ ሕዝባዊ ጥያቄ በማንሳታቸው ምክንያት ከሌሎች የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት ጋር ለእስር ከተዳረጉ እና ከማኅበራዊ ኃላፊነታቸው ከተገለሉ አንድ ዓመት ከ10 ወራት አለፏቸው። ካላ ገዛኸኝ በተከሰሱበት መዝገብ ብቻ 43 ሰዎች ተከስሰዋል። ያነጋገርኳቸው የአካባቢው ነዋሪዎች እንደነገሩኝ ግን የጠቅላላ እስረኞቹ ቁጥር 467 ነው። እነዚህ ሕዝባዊ ጥያቄ ያነሱ የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት በጊዶሌ ማረሚያ ቤት፣ ኮንሶ ፖሊስ ጣቢያ እና አርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ታስረው ይገኛሉ። ካላ ገዛኸኝ እና ሌሎችም 180 ገደማ ሰዎች የታሰሩት በአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ነው። 
ከእስር ውጪ ከመንግሥት የሥራ ገበታቸው ተባርረው (እና ከግንቦት 2008 ጀምሮ) ቤተሰባቸው የኅልውና አደጋ ላይ የወደቀባቸው ከ250 በላይ የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት እንዳሉ ዝርዝሩን እና አቤቱታ ያቀረቡበትን ደብዳቤ ተመልክቻለሁ። 

የኮንሶ ጥያቄ ምንድን ነው?
የአካባቢው ነዋሪዎች እንደነገሩኝ ኮንሶ ተጠሪነቷ ለደቡብ ክልላዊ መንግሥት የነበረች ልዩ ወረዳ ነበረች። ይሁን እንጂ ከመጋቢት 2003 ጀምሮ ልዩ ወረዳነቷ ቀርቶ፣ ተጠሪነቷም ለዞን ሆኗል። ነዋሪዎቹ በአሁኑ ወቅት ‘በሰገን አካባቢ ሕዝቦች’ አስተዳደር ሥር ‘እንደተጨፈለቁ’ የነገሩኝ ሲሆን፣ ይህም የራስን በራስ የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ከመጣሱም በላይ ከተለያዩ የመንግሥት አገልግሎቶች የመገለል ጦስ እንዳመጣባቸው አጫውተውኛል። ይህንንም በመቃወም በ2008፣ የ81ሺሕ ሰዎች ፊርማ በማሰባሰብ 12 አባላት ያሉት ኮሚቴ በመወከል ጥያቄያቸውን ለክልሉ ምክር ቤት እንዲሁም ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርበዋል። ሆኖም ያገኙት መልስ የለም። ይልቁንም የፀጥታ ኃይሎች 12ቱን የኮሚቴ አባላት ሊያስሯቸው ሲሞክሩ ሕዝቡ ሆ ብሎ ወጥቶ በማስቆም፣ የኮሚቴ አባላቱ እንዳይታሰሩ በሚል ውክልናቸውን አንስቷል። 
ኮሚቴዎቹ ቢነሱም ተቃውሞዎቹ ግን የቀጠሉ በመሆኑ በወቅቱ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር የነበሩት አሰፋ አብዩ ተወካዮቻችሁን ላናግር በማለታቸው 23 ሰዎች ተወክለው አነጋግረዋቸዋል። ወትሮም ጥያቄያቸውን ማስተናገድ የነበረበት ሌላ አካል በመሆኑ የፌደራል ፖሊስ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ካላ ገዛኸኝን ጨምሮ ሁሉንም ለቃቅሞ ለእስር ዳርጓቸዋል። በእስሩ ወቅት የጎሳ መሪውን እና ልማዱን በሚያዋርድ መልኩ ካልሞተ በቀር ከክንዱ የማይወልቀውን ከዝሆን ጥርስ እና ከአውራሪስ ቀንድ የተሠራ የቃልኪዳን አምባር ፖሊሶች መሰባበራቸውን በምሬት ነግረውኛል።
ክሱ ምን ይላል?
የታሰሩት ሰዎች ከ400 በላይ ቢሆኑም ፍርድ ቤት እየቀረቡ ያሉት ግን የተወሰኑት ብቻ እንደሆኑ ተነግሮኛል። ፍርድ ቤት ከሚቀርቡት ታሳሪዎች መካከል የነካላ ገዛኸኝ መዝገብ (እዚህ ሙሉውን ማየት ይቻላል) ላይ እንደሚነበበው ከሆነ ክሱ የፖለቲካ ነው። “የወረዳው ሕዝብ በመንግሥት ላይ በአመፅና በአድማ ካልተሰለፈ ይህ ጥያቄ በሠላማዊ መንገድ ምላሽ አያገኝም” በማለት ቅስቀሳ አድርገዋል በሚል ታስረው እስካሁን ፍርድ አላገኙም። እንደሌሎች ፖለቲካ እስረኞችም ክሳቸው አልተቋረጠላቸውም። አሁን ቀጣዩ ቀጠሯቸው በመጪው ሰኞ ሰኔ 18/2010 ነው። 
ለምን አልተፈቱም?
የኮንሶ እስረኞች ከኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች በተቃውሟቸው ምክንያት ተለቃቅመው እንደታሰሩት ዜጎች ሁሉ የፖለቲካ እስረኞች ናቸው። ይሁን እንጂ ከኮንሶ እስረኞች መካከል እስካሁን አንድም ሰው አልተፈታም። በዚህም “እኛ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ወይ?” የሚል ቁጭት ተሰምቷቸዋል። ከ350 ሺሕ በላይ ነዋሪ ባላቸው 42 የኮንሶ ቀበሌዎች የተውጣጡ ሽማግሌዎች ይህንን አቤት ለማለት ተሰብስበው አኔቱታዎቻቸውን ለክልሉ መንግሥትም፣ ለፌዴራሉ መንግሥትም አቅርበው ነበር። ይሁን እንጂ ማንም መልስ አልሰጣቸውም። ይልቁንም አሁንም በክልሉ የፀጥታ ኃይሎች እየተዋከቡ ነው። ከሽማግሌዎቹ መካከል አንድ ሰው ባለፈው ሳምንት ሲታሰር ሌሎችም ማስፈራሪያ እየደረሰባቸው ነው። 
አሁን ዜጎች የፀጥታ ኃይሎች ማዋከብ በመቅረቱ መፍራት ባቆሙበት ሰዐት፣ የኮንሶ ሰዎች ግን አሁንም ከእስር ስጋት ጋር ተፋጥጠዋል። ይህንን እጅግ በጣም አሳጥሬ የጻፍኩትን መረጃ የሰጡኝ ሰዎች ሥማቸውን መጥቀስ ይፈቅዱልኝ እንደሆነ ስጠይቃቸው፣ “እኛ አካባቢ ያለው ሁኔታ እንደ አዲስ አበባ አይደለም። ለኛ ጥሩ አይደለም” ብለውኛል። 
ለኮንሶ ብሔረሰብ ዜጎቻችን የሚደርስላቸው ማን ይሆን? [እባካችሁ ይህንን መረጃ እንዲሰራጭ በማገዝ የሚመለከተው አካል በአስቸኳይ የኮንሶ ዜጎቻችንን ከእስር እንዲፈታ የበኩሎን አስተዋፅዖ ያድርጉ።]

(ከታች ያስቀመጥኳቸው ጥቆማዎች በጥናት ላይ የተመሠረቱ የመፍትሔ ሐሳቦች ሳይሆኑ በግል ትዝብት የተጠቆሙ ናቸው። በምስሉ ላይ የሚታየው (ፎቶ: ቴዎድሮስ አያሌው) በ1977 ድርቅ ወቅት ደርግ ቄለም ወለጋ አስፍሯቸው የነበሩ እና አሁን ተፈናቅለው አላማጣ የሚገኙ ናቸው። በምስሉ እንደሚታየው አብዛኛዎቹ የተወለዱት እዚያው አካባቢ ሲሆን፣ ወላጆቻቸው እና አያቶቻቸው ናቸው ከአላማጣ ነበር ቄለም ወለጋ እንዲሰፍሩ የተደረጉት።)

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ‘የማንነት’ እና ‘የብሔር’ ፖለቲካ ወይም ጥያቄ ተምታተዋል። ብዙ ግዜ ሁሉም ነገር ‘የብሔር ጥያቄ’ ነው፤ መልሱም የሚገኘው ‘በብሔርተኝነት’ ነው የሚባለው ጉዳይ ከማንነት ጋር የተያያዘውን ጥያቄ ያድበሰብሰዋል። እንዲያውም አንዳንዴ ብሔርተኝነት ችግሩን ሊያባብሰው ይችላል። የማንነት ወይም የብሔር ትርጉሙም እንዲሁ የተምታታ ነው። ምክንያቱም ማንነትም ይሁን ብሔር በተለምዶ የሚበየነው በቋንቋ ላይ ተመሥርቶ ነው። ስለዚህም በተምታታ ትርጉም ላይ የተመሠረተ ብሔርተኝነትም ለተሳሳተ ጥያቄ የተሳሳተ መልስ ለመስጠት ይዳርጋል። ማንነት በቋንቋ ሊመሠረት ይችላል፤ ነገር ግን አንድ ቋንቋ እየተናገሩ የተለያየ ማንነት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ሕዝቦች አሉ። ማንነት በፆታ ብቻ ሊወሰን ይችላል። ወይም ደግሞ በፆታዊ ግንኙነት ምርጫ ሊወሰን ይችላል። በመልክ ወይም በቆዳ ቀለም። ወዘተ… ለምሳሌ ያክል ቱትሲዎች እና ሁቱዎች አንድ ቋንቋ ተናጋሪ ሆነው፣ ልዩነታቸው የመልክ (እና የታሪክ ድርሻ) ነው። 
ፌዴራሊዝሞች የአወቃቀር ስርዓታቸው ምንም ቢመስል፣ ዋነኛ ዓላማቸው በብሔርተኝነቶች መካከል ውጥረቶችን ሥልጣን በማከፋፈል እና በማጋራት ማርገብ ነው። የእኛው ግን ውጥረቱን ምናልባትም አባብሶታል አልያም ገሀድ አውጥቶታል። በሕገ መንግሥቱ ባይሰፍርም “የእንትን ክልል፣ ለእነ ‘እንቶኔ'” የሚል ያልተጻፈ ሕግ አለ። ‘እንቶኔነት’ ከወላጆች በደም የሚወረስ መሆኑም እንዲሁ ያልተጻፈ ሕግ ነው። ስለዚህ በእንትን ክልል ያሉ ከእነ እንቶኔ ውጪ ያሉ ነዋሪዎች በሙሉ የመገለል፣ የመጠቃት፣ የመሰደድ ዕድላቸው ሰፊ ነው። በእርግጥ በዚህ መሰሉ ጥቃት እና ስደት በተደጋጋሚ የሚጠቁት ሰዎች በተለይ በብዙ ክልሎች የተበተኑት ብሔረሰብ አባላት ናቸው። ነገር ግን ይሔ ዕጣ ያልገጠመው አለ ለማለት ይከብዳል። ባለፈው ዓመት ከሶማሌ የተፈናቀሉት 600 ሺሕ የኦሮሞ ተወላጆች ጉዳይ ሪከርድ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ የአማራ ተወላጆች የመፈናቀል ዜናን መስማትም ለጆሮ እንግዳ አይደለም። የሆነ ሆኖ ዛሬ በኢትዮጵያ ያሉ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች ቁጥር 1 ሚሊዮን ተኩል ገደማ ነው። በየዘውጉ ተጎራባቾች አንዱ አንዱን በውኃ እና ግጦሽ/እርሻ መሬት ማጥቃት እና ማፈናቀል የነበረ፣ እና የበለጠ ፖለቲካዊ እየሆነ የመጣ ነገር ነው። ማንነትን መሠረት ያደረጉ መፈናቀሎች በተከሰቱ ቁጥር የዘውጉን ቡድን እየቆጠሩ የአንድ ወገን ጉዳይ ብቻ ማስመሰሉ ለብሔተኝነት ፖለቲካ ይበጅ ይሆናል እንጂ ችግሩን ለመቅረፍ እምብዛም አይበጅም። ልብ በሉ፣ የተፈናቀሉት ሰዎች በማንነታቸው እስከሆነ ድረስ የተፈናቃዮቹን ማንነትም ይሁን የአፈናቃዮቹን ማንነት መጥቀሱ ላይ ችግር የለውም። ነገር ግን ለብሔርተኝነት ትርፍ ሲባል ብቻ ነገሩ በሁለት ሕዝቦች መካከል የተደረገ ፍጥጫ ማስመሰል እሳቱ ላይ ነዳጅ ማርከፍከፍ ነው። ከዚያም በላይ ሰዎች ችግሩን በገለልተኛ ዓይን አይተው እንዳይከላከሉት ወይም ጥብቅና እንዳይቆሙለት ይገፋል።
ለምሳሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝ ክልል አንድ ቀበሌ ውስጥ የተፈናቀሉ የአማርኛ ተናጋሪዎች ጉዳይ “የቤንሻንጉል-ጉሙዝ ሕዝብ የአማራን ሕዝብ አፈናቀለ” ብሎ መዘገብ የተሳሳተ ምስል ከመስጠቱም በተጨማሪ በሁለቱ ሕዝቦች መካከል መቃቃር ይፈጥርና በክልሉ ሌሎች ቀበሌዎች ነዋሪዎች የሆኑ አማርኛ ተናጋሪዎችንም ለበለጠ ጥቃት ሊዳርግ ይችላል። አንዳንዴ መፈናቀሎቹ የሚከሰቱት በቀበሌዎቹ አስተዳደሮች ሆኖ ሳለ፣ የሕዝቡ ሥራ አስመስሎ ማቅረቡም ነዋሪዎቹን ከጎረቤቶቻቸው ጋር ማቀያየም ነው።
ችግሩ እንዴት ይቀረፍ?
በመጀመሪያ ደረጃ የችግሩን ምንጭ በአግባቡ መፈተሽ አስፈላጊ ነው። ዋነኛው ችግር የሚመስለኝ የአስተሳሰብ ነው። 
1ኛ፣ ክልሎች የየትኛውም ክልል ተወላጅ በክልላቸው የመኖር መብት እንዳለው መቀበልና መብቱን ማረጋገጥ አለባቸው።
የትኛውም ክልል የየትኛውም ብሔረሰብ ተወላጅ የግል ንብረት አይደለም። የትኛውም ብሔረሰብ ተወላጆች በየትኛውም ክልል ውስጥ ከየትኛውም ብሔረሰብ ተወላጅ የበለጠ ወይም ያነሰ መብት የላቸውም። የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 32/1 “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወይም በሕጋዊ መንገድ ሀገሪቷ ውስጥ የሚገኝ የውጭ አገር ዜጋ በመረጠው የአገሪቱ አካባቢ የመዘዋወርና የመኖሪያ ቦታ የመመሥረት፣” መብት አለው ይላል። ይህ ደግነቱ ሕገ መንግሥቱ አክብሮታል አንጂ ባያከብረውም የማይሻር የተፈጥሮ ሕግ ነው። በክልሎች ቀርቶ በአገራት ድንበሮች ይህንን መገደብ ከተፈጥሮ ሕግ ያፈነገጠ፣ ነገር ግን ለስርዓት (order) ሲባል የምንታገሰው ሕግ ነው። ይህንን ከልብ መቀበል ያስፈልጋል። በሕግ እና ደንቦች የሚተገበርበት መንገድ ይመቻቻል እንጂ በልዩነት የሚታደልበት/የሚነፈግበት መንገድ ሊኖር አይገባም። 
ፌደራሊዝሙ ያልተማከለ አስተዳደር ፈጥሯል። (በፌዴራሊዝሙ አወዛጋቢው ጉዳይ አከላለሉ ዘውግ-ተኮር መሆኑ ላይ ነው። ይሔ ጽሑፍ መዋቅሩ ሳይለወጥ ችግሩን መቅረፍ ላይ ያተኮረ ስለሆነ ወደዛ ውዝግብ አንገባም።) እነዚህ አስተዳደሮች በእየርከኑ ባሉ የአስተዳደር ክፍሎች ውስጥ የነዋሪዎችን ቁጥር ከግምት ውስጥ ያስገባ የብዙኃን አመራር እና የድሀጣንን መብት የማክበር ግዴታ አለባቸው። ብዙኃኑ የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ከሆነ ቋንቋው የክልሉ የሥራ ቋንቋ ባይሆን እንኳ የአስተዳደር ክፍሉ የሥራ ቋንቋ መሆን ይኖርበታል። ይህ ግን ለአስተዳደር ቅልጥፍና እንጂ መብትን ለማከፋፈል አይደለም። ድሀጣኑ ከብዙኃኑ ዕኩል መብቶች እና ዕድሎች ሊኖሯቸው የግድ ነው። በሕጋዊ መንገድ መኖሪያ ቦታ የማግኘት እና የመሥራት መብታቸው ያለቁጥራቸው ወይም ያለማንነታቸው ገደብ ሊከበርላቸው ይገባል። የአካባቢ አስተዳደሮች ይህ አረዳድ እንዲሰርፃቸው ያልተቋረጠ የብዙኃን መገናኛዎች ዘመቻ እና የግንዛቤ ማስበጫ ሥልጠናዎች ሊሰጧቸው ይገባል። (በነገራችን ላይ በብዙ ክልላዊ አስተዳደሮች ውስጥ በርካታ አማርኛ ተናጋሪ ነዋሪዎች ያሉ ቢሆንም፣ ከአማርኛ ተናጋሪዎቹ ቁጥር ያነሰ ተናጋሪ ያላቸው ቋንቋዎች የሥራ ቋንቋ ሳይሆኑ ሌሎቹ የሆኑበት ብዙ ምሳሌ አለ። የአማርኛ ተናጋሪዎቹ ቁጥር እና አሰፋፈር እስከፈቀደ ድረስ ልዩ የአስተዳደር ዞን፣ ወይም ተደራቢ የሥራ ቋንቋ መሆን የማይችልበት ሕጋዊ አግባብ የለም።)
2ኛ፣ ከትውልድ ክልላቸው ውጪ የሚኖሩ ግለሰቦች የሚኖሩበትን ክልል ሕግ እና ደንቦች (ፍትሓዊ ወይም በሁሉም ላይ የተጣሉ እስከሆኑ ድረስ) ማክበር አለባቸው። 
አንዳንድ ከትውልድ ቀዬአቸው ውጪ የሚኖሩ ዜጎች፣ ማኅበረሰቤ ብለው የሚጠሩት የተወለዱበትን እንጂ የሚኖሩበትን ቀዬ አይደለም። ይባስ ብሎ የተወለዱበት፣ ያደጉበትን ቀዬ ሳይሆን የወላጆቻቸውን ደም እና የትውልድ ቀዬ ቆጥረው ቀዬዬ ብለው የሚጠቅሱ አሉ። “የኔ” የሚሉትን ማኅበረሰብ መምረጥ የግል ድርሻቸው ቢሆንም የሚያስከፋው ነገር የሚኖሩበትን ማኅበረሰብ የሚንቁ ሰዎች መኖራቸው ነው። እነዚህኞቹ፣ በሚኖሩበት አካባቢ የአስተዳደር ችግር ሲደርስባቸው ‘አቤት’ የሚሉት ለሚኖሩበት ክልል አስተዳደር የላይኛው ክፍል ሳይሆን፣ ለመጡበት ክልል አስተዳደር ነው። ይህ ያልተማከለ አስተዳደር የሥልጣን ክፍፍልን የሚጋፋ እና በክልሎች መካከል ውጥረት የሚያነግሥ አካሔድ ነው። በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል አንድ ቀበሌ ውስጥ አስተዳደራዊ በደል የደረሰባቸው ዜጎች፣ ከዚያ በላይ ላለው አስተዳደር ወይም ፌዴራል መንግሥቱ ያመለክታሉ እንጂ ለመጡበት/ለሚወለዱበት ክፍል ማመልከት የለባቸውም። 
ዜጎቻችን አገር ለቀው ሲወጡ፣ የሚቀበላቸውን አገር ባሕልና ስርዓት አክብረው እንደሚኖሩ ሁሉ፣ በአገር ውስጥ ከአንዱ ቀዬ ወደሌላው ሲሔዱ፣ አዲስ ለሚኖሩበት አካባቢ ልማድ እና አሠራር (መሠረታዊ መብቶቻቸውን እስካልገፈፉ ድረስ) ተገዢ መሆን ይኖርባቸዋል። የአካባቢውን ደንብና ስርዓት አለማክበር የግጭት እንዲሁም የመፈናቀል መንስዔ ስለሆነ በዚህ መንገድ መከላከልም ይቻላል።
3ኛ፣ ብሔርተኞች ብሔርተኝነት በዘውግ ሳይሆን በክልል ላይ አስተሳሰቡን እንዲወስን ማድረግ አለባቸው። 
ይህ የዘውግ ብሔርተኝነት (ethno-nationalism) ከክልሎቹ ሥያሜ ይጀምራል። አማራ፣ ሶማሊ፣ አፋር፣ ሐራሪ፣ ቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልሎች ለምሳሌ በክልሎቹ በሚኖረው አብዛኛው ሰው ዘውግ ሥያሜ ነው ክልሎቹ የሚጠሩት። ከዚህ በተሻለ ኦሮሚያ፣ ትግራይ፣ ጋምቤላ እና ደቡብ ሕዝቦች ዐቃፊ አገላለጽ አላቸው። ይሁን እንጂ እነርሱም ብሔርተኝነታቸው ክልላዊ (territorial-nationalism) አይደለም። ለምሳሌ በኦሮሚያ ገዢው ፓርቲ ኦሕዴድ (የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት) እንጂ “የኦሮሚያ ሕዝቦች” አልተባለም። በኦሮሚያ የሚኖሩት ግን የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች ብቻ ባለመሆናቸው ዐቃፊነት ይጎድለዋል። በዚያው ክልል ተቃዋሚው ኦፌኮ (የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ) ነው። የኦሮሚያ አለመሆኑ ብሔርተኝነቱ በክልሉ ያሉትን ሌሎች ዘውጎች እንዳያቅፍ ከሥሙ ጀምሮ እንቅፋት ይሆናል። የሌላ ዘውግ አባላት ለመብቶቻቸው ለመታገል እነዚህን ድርጅቶች መቀላለቀል አይችሉም ማለት ነው። በብአዴንም ተመሳሳይ ችግር ነው የምንመለከተው። በትግራይ አረና ምንም እንኳን በተግባር ባይሳካለትም በአስተሳሰብ ደረጃ ክልላዊ ፓርቲ ነው። የክልሉ ነዋሪ እስከሆኑ ድረስ ትግራዋይ ያልሆኑ ሰዎችም አረናን መቀላቀል ይችላሉ። 
ብሔርተኝነትን ክልላዊ ማድረግ በክልሉ ውስጥ ከብዙኃኑ ዘውግ ያልተወለዱ ሰዎች በክልሉ ውስጥ ውክልና እንዲኖራቸው ያደርጋል። ብዙዎቹ መፈናቀሎች የሚከሰቱት ሰዎቹን የሌላ ክልል ሰው ናቸው ብሎ ከሚያስብ በመነጨ አስተሳሰብ ነው። ነገር ግን ሰዎች አንድን አካባቢ መርጠው በሕግ አግባብ ነዋሪ እስከሆኑ ድረስ መወከል የሚኖርባቸው በሚኖሩበት አካባቢ እንጂ ጥለውት በመጡት አካባቢ መሆን የለበትም። ብሔርተኝነት ክልላዊ ሲሆን በነዋሪዎቹ መካከል ያለውን የዘውግ ውጥረት ይቀንሳል። ለምሳሌ ያክል በኦሮምያ ክልል ላሉ አማራዎች የአማራ ክልል ብሔርተኝነት ነው ጥብቅና የኦሮሚያ ብሔርተኝነት እንዲሆን ያደርጋል። 
4ኛ፣ የፌዴራል መንግሥቱ ከቀዬ ለመሰደድ እና የአገር ውስጥ ፍልሰት ፖሊሲ መቅረፅ አለበት። 
አዲስ አድማስ ጋዜጣ የጠየቃቸው አንድ ተፈናቃይ ወደትውልድ መንደራቸው ለምን እንደማይሔዱ ሲናገሩ ከትውልድ ቀያቸው የተሰደዱት የእርሻ መሬት አጥተው እንደሆነ ተናግረዋል። በርግጥም የአገር ውስጥ ፍልሰት ዋነኛው መንስዔ የእርሻ መሬት ለልጅ ልጆች ሲተላለፍ እየጠበበ ቤተሰብ ማስተዳደር ባለመቻሉ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ብዙ ግዜ በመታረሱ መሬቱ እየነጠፈ ራሳቸውን ለማስተዳደር ሌላ ቦታ ሔደው ማረስ ስለሚገደዱ ነው። እነዚህ ከቀያቸው በችግር የፈለሱ ዜጎች ሌሎች መንደሮች እየሔዱ ጫካዎችን በመመንጠር፣ የግጦሽ መሬቶችን በመውረር እና በሌሎችም ሕጋዊ በሆኑና ባልሆኑ መንገዶች የሚቀይሱት መንደር ከሔዱበት አካባቢ ሰዎች ጋር ግጭት ውስጥ እየከተታቸው ነው። ስለሆነም ይህ ችግር እየተባባሰ ይሔድ እንደሆነ እንጂ እየቀነሰ የሚሔድ አይመስልም። ሆኖም የፌዴራል መንግሥቱ ይህንን ጉዳይ አቅጣጫ ለማስያዝ የሚያስችል ፖሊሲ የለውም። ችግሩ አንድም ከሕዝብ ብዛት ጋር የሚያያዝ ነው። ይሁን እንጂ ያለፉት ሁለት የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዶች የሕዝብ ብዛትን በተመለከተም ይሁን የአገር ውስጥ ፍልሰትን በተመለከተ ያስቀመጡት አቅጣጫ የለም። ይህ ለቀውሱ መባባስ ብቻ ሳይሆን አፋጣኝ የእርምት እርምጃ መውሰድ እንኳን እንዳይቻል አድርጓል። 
5ኛ፣ መጠባበቂያ ፈንድ መመደብ።
ምንም እንኳን ዋናው ሥራ መፈናቀልን መከላከል ቢሆንም ከሆነ በኋላም ሰብአዊ እርዳታ ለተፈናቃዮቹ በአስቸኳይ ሊደርስላቸው ይገባል። በበጀት ረገድ ምን እየተሠራ እንደሆነ አላውቅም። የሆነ ሆኖ የዘንድሮን ያክል የከፋ ባይሆንም መፈናቀል በእየዓመቱ እየተከሰተ ነው። በአሁኑ ወቅት ብዙዎቹ ተፈናቃዮች በጊዜያዊ መጠለያዎች ውስጥ ናቸው። ግዜያዊ መጠለያዎቹ መሠረታዊ ፍላጎቶቻቸውን ለሟሟላት እንኳ አይችሉም። የንፅህና መጠበቂያ እና መፀዳጃ ሥፍራዎች አልተመቻቹላቸውም። ከምግብና መጠጥ እጥረቱ በተጨማሪ መሠረታዊ የሕክምና አገልግሎት ማግኘት የማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ናቸው። በዚያ ላይ ጊዜያዊ መጠለያዎቹ ውስጥ ሳይገቡ በአካባቢው ሰዎች ተጠግተው የሚኖሩም አሉ። ከችግሩ አሳሳቢነት አንፃር መንግሥት መጠባባቂያ በጀት በዚህ ሥም ማዘጋጀት እና የሰብአዊ እርዳታ ማድረግ እንዲሁም መልሶ ማቋቋም ይኖርበታል። 

ኦሕዴድ እና ብአዴን በሕወሓት የበላይነት ይመራ የነበረውን የኢሕአዴግ ፖለቲካ ከውስጥ መነቅነቅ ሲጀምሩ ተቃዋሚዎች ተደስተው ነበር። ኦሕዴድ በክልሉ አንፃራዊ የተቃውሞ-ነጻነት ሲፈቅድም እንዲሁ ተደስተዋል። ነገር ግን የዐብይ ጠቅላይ ሚኒስትርነት እና የተቃዋሚውን ቋንቋ መነጋገራቸው ድንጋጤ ፈጥሯል። ባጭሩ ተቃዋሚዎች ከኢሕአዴግ ጋር “መደራደር ይገባናል” ሲሏቸው የነበሩት ጉዳዮች – የፖለቲካ እስረኛ ማስፈታት እና አንዳንድ አዋጆችን ማሻሻል፣ በጥቅሉ የፖለቲካ ምኅዳሩን የማስፋት ጥያቄ እና ተቋማትን ከፖለቲካ ጥገኝነት ማላቀቅ – የመሳሰሉትን ነገሮች በራሳቸው በኢሕአዲጉ ሊቀ መንበር ሲቀነቀን፣ ተቃዋሚዎች አጀንዳ አጥተዋል። የድንጋጤያቸው ምንጭም ይኸው ይመስላል። በርግጥ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ሲያልፉበት ከነበረው ፈታኝ ሁኔታ አንፃር በመዳከማቸው የፖለቲካ ለውጦችን እያዩ ከወቅቱ ጋር የሚሔድ ፖለቲካ መጫወት ቢያቅታቸው የሚገርም አይደለም። 
የፖለቲካ ድርጅቶቹ “የአኩራፊዎች እና የጡረተኞች መሰብሰበቢያ” እየተባሉ ሲተቹ ከርመዋል። ምንም እንኳን ከላይ ያሉ ቢመስልም ውስጣቸው በብዛት ባዶ ነው። ለኢትዮጵያ (100 ሚሊዮን ሕዝብ) የሚመጥን የመምራት አቅም ያላቸው ሰዎች ስብስብ የላቸውም። በመገናኛ ብዙኃን በሚራገቡ አጀንዳዎች ላይ የመንግሥትን አቋም ካወቁ በኋላ ተቃራኒውን ይዘው ከመሟገት በላይ ርዕዮተ ዓለማዊ አቅጣጫ የሌላቸው ድርጅቶች ቀላል አይደሉም። አንዳንዶቹ ከላይ ያሉትን ታዋቂ ሊቀ መንበሮቻቸውን የሚተኩ አባላት እንኳን አላፈለቁም። ኢትዮጵያን መምራት የሚችሉ በርካቶች ድግሞ ወይ የፖለቲካውን ትኩሳት እየፈሩ አንገታቸውን ደፍተው ‘ዝምተኛ-ብዙኃን’ መሐል ተቀብረዋል፤ አልያም ተሰድደዋል። በዚህም ምክንያት ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶቹ የኢሕአዴግ የፖለቲካ አጨዋወት ሲቀየር፣ የራሳቸውን አጨዋወት በመቀየር ፈንታ ድንጋጤ ውስጥ መግባታቸውን የሚያሳብቁ ነገሮች ናቸው አሁን የሚታዩት። “እስረኛ የፈቱት ወደው ሳይሆን ተገደው ነው”፣ “ሰውዬው ኢሕአዴግ ናቸው፣ ኢሕአዴግ ከሚቀየር ግመል በመርፌ ቀዳዳ…”፣ “ጥቂት ሰዎች ተቀየሩ ማለት ነገሮች ተቀየሩ ማለት አይደለም”፣ “ይች ይቺ ተቃውሞ ለማስቆም የተፈጠረች የኢሕአዴግ ሴራ/ድራማ ናት”… እነዚህ ንግግሮች ለቀጣዩ የፖለቲካ ጫወታ ፋይዳቸው ምን እንደሆነ ሊገባኝ አይችልም። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በእያንዳንዱ ንግግራቸው እና ድርጊታቸው የብዙዎችን ቀልብ እየገዙ እና “አለቀለት” ለተባለው ኢሕአዴግም አዲስ ነፍስ እየዘሩበት ነው። ይህ የገባቸው ተቃዋሚዎች የማጥላላት እና የማጣጣል ትርክት ለመፍጠር እየተፍጨረጨሩ ነው። ይህ ፖለቲካዊ ኪሳራ ሊያስከትል ይችላል።  የሴራ ፖለቲካዊ ትንተና እና ጫወታም መሬት ላይ ጠብ የሚያደርገው እንደሌለ ከበቂ በላይ ታይቷል። የብሽሽቅ ፖለቲካም ጉንጭ ከማልፋት በላይ ትርፍ የለውም። ሕዝብን “ተታልላችኋል” እያሉ መውቀሱም አግባብ አይደለም። ምክንያቱም ሕዝቡ የሚያየውን መዳኘት ይችላል።
ይልቁንም (በፖለቲካ ምኅዳሩ መጥበብ ምክንያት የተከተለው እና ሁለተኛው ደረጃ) “የማማረር ፖለቲካ” ተላቅቆ፣ ወደ አንደኛው ደረጃ ፖለቲካ ማለትም አማራጭን የማሳየት እና ሕዝባዊ መሠረት የመጣል ፖለቲካ መጫወት ያስፈልጋል። የፖለቲካ ምኅዳሩ ለይቶለት ሳይዘጋ በፊት ለእስር እና ስደት የተዳረጉት ፖለቲከኞች ጥያቄ ምንድን ነበር? የሕዝቦች ጥያቄ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ደኅንነት እንዴት ነው የሚጠበቀው? ድንቁርና እና ድህነትን እንዲሁም ኢፍትሓዊነትን ለመቀነስ አገራችን ምን ዓይነት የፖለቲካ ስርዓት መከተል አለባት? አሁን ሰዐቱ ይህንን የመመለስ ነው። 
የፖለቲካ ድርጅቶች የሚሠሩት ሥራ በየአደባባዩ ሰልፍ ከመውጣት እና የተቃውሞ መግለጫዎችን ከማውጣት በላይ ነው። አብላጫ የምክር ቤት ወንበር አግኝተው መንግሥት ሲመሠርቱ ብቻ ሳይሆን፣ እንደ አማራጭ በመኖራቸው ብቻ የሚሠሯቸው ሥራዎችም ብዙ ናቸው። በዋነኝነት አማራጭ የአገር አመራር አቅጣጫ ማሥመር አለባቸው። አገሪቱ ወዴት ነው መሔድ ያለባት? እንዴት ነው ወደዚያ መሔድ የምትችለው? የሚሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚያስችሉ የማኅበረ–ኢኮኖሚያዊ ፍልስፍናቸውን ለሕዝብ ማስተዋወቅ አለባቸው። ለዚህ ደግሞ ብቁ የሆኑ አመራሮችን መሰብሰብ እንዲሁም እየኮተኮቱ ማሳደግ አለባቸው። አለበለዚያ እንደሥማቸው ተቃዋሚ ብቻ ሆነው ይቀራሉ። 
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ “ተፎካካሪ” የሚለውን መጠሪያ እንደአስታራቂ መርጠዋል። እኔ እስካሁን ያለውን ፖለቲካ የገዢ እና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፖለቲካ ብለው እመርጣለሁ። ምክንያቱም ገዢው ፓርቲ አገር ለመምራት ወይም ሕዝብ ለማገልገል ሳይሆን ፈላጭ ቆራጭ ገዢ ለመሆን ነው ሲተጋ የኖረው። ተቃዋሚዎች ደግሞ የገዢውን አገዛዝ ሲቃወሙ እዚህ ደርሰናል። ኢሕአዴግ መቀ:የር እፈልጋለሁ ብሎ ጭላንጭል ሲያሳይ፣ የነገውን ለነገ ትተው ተቃዋሚቹም መቀየር አለባቸው። እውነተኛ አማራጭነታቸውን ለማሳየት አጋጣሚውን መጠቀም ይኖርባቸዋል። አለበለዚያ ነገ ኢሕአዴግ ስህተት እስኪሠራ ጠብቆ “ይኸው ይሄንኑ ፈርተን ነበር” ማለት አያዋጣም፤ በሥሙ ብዙ ነገር ለሚፈፀመው ሕዝብም የሚያተርፍለት ነገር የለም። ምንም እንኳን ወደፊትም የመሔድ ወይም ወደ ኋላ የመመለስ ዕድሉ ዕኩል ቢሆንም አሁን (በዚህ ቅፅበት) ከሞላ ጎደል ሰፊ የፖለቲካ ምኅዳር አለ። የፖለቲካ ምኅዳሩ ስፋት ወደኋላ እንዳይመለስ ሕጋዊ እና ተቋማዊ መሠረት አፍርቶ ለዘለቄታው ዋስትና እንዲያገኝ ከመሥራት ጎን ለጎን አማራጭ የፖለቲካ መፍትሔን ለሕዝብ ማስተዋወቅ ያስፈልጋል። ሕዝብ ውስጥ የሰረፀ ፖለቲካዊ የመፍትሔ ሐሳብ ካለ፣ አመንጪዎቹ የፖለቲካ ድርጅቶች ባይኖሩም እንኳን የግዜ ጉዳይ ቢሆን ነው እንጂ ግቡን ይመታል።
አማራጭ የፖለቲካ ሐሳብ ያላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ካሉ እኛም “ገዢ” እና “ተቃዋሚ” እያልን ከመፈረጅ እንገላገላለን። “ተፎካካሪ” ከሚለው እና የሥልጣን ሽሚያን ብቻ ከሚጠቁመው ቃልም ይልቅ “አማራጭ” የፖለቲካ ድርጅቶች የሚለውን እንጠቀማለን። አማራጭ የፖለቲካ ድርጅቶች ካሉ፣ የድርጅቶቹን ሥም ስንሰማ የገዢውን ሐሳብ በመቃወማቸው ሳይሆን፣ በአማራጭ ሐሳባቸው እናስታውሳለቸዋለን። ‘ምረጡን’ ብለው ሲመጡም እንደተቃዋሚ “ተቃውሟቸውን” ወይም እንደ ተፎካካሪ “ፉክክራቸውን” ሳይሆን አማራጭ ሐሳባቸውን እንመርጣለን። 
Time to move on, and choose your place in the board. 

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ተስፋን-በጥንቃቄ (cautious optimism) ካነገቡት ሰዎች አንዱ ነኝ። የተስፋዬ መሠረቶች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን የመጡበት መንገድ፣ የገቧቸው ቃልኪዳኖች እና አሁን የታየው መረጋጋት ናቸው። አሁን የታየው መረጋጋት ስል የቄሮዎች የአደባባይ ተቃውሞ መቆሙን ማለቴ አይደለም። ተቃዋሚዎችን እያሳደዱ መከታተል፣ ማዋከብ እና ማሰር ርቀን ሳንሔድ አምና ከነበረው አንፃር እንኳ ልዩነቱ የትየለሌ ነው። ለዚህ የራሴን ስሜት እና ተሞክሮ ነው በምሳሌነት የማቀርበው። በፊትም አሁንም ሐሳቤን በነጻነት እገልጻለሁ። ነገር ግን አምና እና ካቻምና ከያንዳንዱ ጽሑፎቼ/ንግግሮቼ ቀጥሎ እስር ይመጣል እያልኩ እየሰጋሁ ነበር የማደርገው። አሁን ምን ያክል ይዘልቃል የሚለው ቢያሰጋኝም እታሰራለሁ እያልኩ በየደቂቃው አልባትትም። በፊት ሲያስሩ፣ ሲያዋክቡ እና ሲከስሱ ከነበሩት አንዳንድ ኃላፊዎችም ጋር ባጋጣሚዎች አውርቻለሁ። ከላይ ለውጥ ያለ ሲመስል እነርሱም ከታች ይለወጣሉ። አንድ ከፍተኛ የፌዴራል ፖሊስ ኃላፊ የኛን እንቅስቃሴ “የበፊቱ አመራር እንደ ወንጀል ያየው ስለነበር ወንጀል ነበር። አሁን ግን እንደወንጀል አይታይም” ብለውኛል። ይህ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሰዎች ላይ የተፈጠረው የ”ለውጥ መጥቷል” ስሜት እና የፍርሐት ማጣት ከተጠቀሙበት ለጠቅላይ ሚኒስትሩም ትልቅ ዕድል ነው። ሌላው ሌላው ሁሉ ለዘለቄታው ለመቅረፍ ረዥም የፖለቲካ እና የሥራ ባሕል አብዮት የሚፈልግ ፈርጀ ብዙ የሁላችንም ችግር ነው።
አሁን ስጋቴ ከግዜ ጋር የሚደረገው ፉክክር ነው። ጊዜ መጨቆኛ መዋቅሩን ለተቆጣጠሩት ጨቋኞችም፣ ባዶ እጃቸውን ለገጠሟቸው ተጨቋኞችም ዕኩል ነው የሚነጉደው። ማርቲን ሉተር ኪንግ (ትንሹ) “ጊዜ ከደጋጎች ይልቅ ክፉዎቹ የተሻለ የሚጠቀሙበት ይመስለኛል” ብሎ ጽፎ ነበር። ለዚህ ነው ማንም መጣ ሔደ ለመሪዎች ለውጥ ማስኬጃ በሚል ሰበብ አላግባብ ጊዜ መሸለም የማያስፈልገው። እውነተኛው ለውጥ በተቋማት ለውጥ እንጂ በሰዎች ለውጥ አይመጣምና! 
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ትልቁ ተልዕኮ የ2012ቱ የኢትዮጵያ አገር ዐቀፍ ምርጫ ነጻ እና ርትዓዊ እንዲሆን ማድረግ ነው ብዬ አምናለሁ። ነገር ግን ይህን “ብዙ መጠበቅ” ነው ብለውታል የኢትዮጵያን ጉዳይ በመተንተን የሚታወቁት ፈረንሳዊው ሬኒ ሊኾርት። እሳቸው እንደሚሉት ኢሕአዴግ የውስጥ ልዩነቱን ፈትቶ ሠላም ካላላገኘ፣ አገሪቱም ሠላም አታገኝም። ተረኩ የፓርቲውን መበተን ከኢትዮጵያ መበተን ጋር የሚያስተካክል ነው። የፓርቲው አባላት ሁሉንም ክልላዊ መዋቅሮች በተቆጣጠሩበት እንዲሁም አማራጭ የተደራጁ ኃይሎች በሌሉበት ሁኔታ ይህ አይሆንም የሚባል አይደለም። ነገር ግን ይህ የኢሕአዴግ ውስጣዊ ክፍፍል ተቀርፎ የሥልጣን መደላድል ከመጣ ሁሉም ነገር ወደነበረበት የጭቆና አዙሪት ይመለሳል የሚል ስጋት አለኝ። 
የጠ/ሚኒስትሩ የሥልጣን ምንጭ ምንድን ነው?
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ በኢሕአዴግ ውስጥ የተቃዋሚውን ቋንቋ በመናገር ነው ለሥልጣን የበቁት። በዝግ ስብሰባቸው ምን እንደተመከረ፣ ምን ዓይነት የማመቻመቻ ድርድር/ቃልኪዳን አድርገው አብላጫ ድምፅ ለማግኘት እንደቻሉ አናውቅም። ዞሮ ዞሮ መርጠው ለዚህ ያበቋቸው የኢሕአዴግ አባላት ናቸው። የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር (ኃይለማርያም ደሳለኝ) ያለግዜያቸው እንዲለቁ፣ እሳቸውም ከኢሕአዴግ ባፈነገጠ አካሔድ የኢሕአዴግን ሥልጣን እንዲቆናጠጡ ያደረጋቸው ሕዝባዊ ተቃውሞ ነው። ስለዚህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥልጣን ምንጭ ኢሕአዴግ እና ሕዝባዊ ተቃውሞዎች በጣምራ ነው።  ይህ በሥልጣን ዘመናቸው ሊሠሩ የሚችሉትን ማመላከቻ ነው። በርግጠኝነት ኢሕአዴግን ማፍረስ አይፈልጉም፤ ምናልባት ማደስ ግን ይፈልጋሉ። በምን ዓይነት መንገድ? ምናልባትም ሕዝባዊ ጥያቄዎችን በመመለስ። ተቃርኖው የሚጀምረው እዚህ ጋር ነው። 
የኢሕአዴግ (አብዮታዊ ዴሞክራሲ) ትልቁ ችግር ሕዝባዊ ጥያቄዎችን በራሱ አውጥቶ፣ መልሱንም በራሱ መንገድ መስጠት ነው።  ዴሞክራሲ ደግሞ በተቃራኒው ሕዝብ ችግሩን እንዲናገር በመፍቀድ እና ችግሩን በመቀበል፣ መፍትሔው ከሕዝቡ ፍላጎት አኳያ እንዲመለስ ማድረግ ነው። ይህ ሕዝባዊ ቅቡልነት የሚያስገኝ አሠራር ግን የኢሕአዴግን ሕልውና አደጋ ላይ ሊጥልበት ይችላል። ስለዚህ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በልባቸው የያዙት፣ በቅንነት የተመራ የለውጥ ፍላጎት ካለ ይህንን ፈተና ለመጋፈጥ መዘጋጀት አለባቸው። የሕዝብ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ያለባቸው መልሶቹ ኢሕአዴግን ወደመቃብር የሚልኩት ቢሆንም እንኳን ነው። ይህ ግን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢስማሙባቸው እንኳ በዝግ መክረው ለመረጧቸው የኢሕአዴግ አባላት የሚያስማማቸው ይመስላችኋል? እኔን ያጠራጥረኛል።
በ2012 ነጻ እና ርትዓዊ ምርጫ ለማድረግ ከሚያስፈልጉት ነገሮች ውስጥ ዋነኛው ሜዳውን ለሁሉም ዕኩል ማደላደል እና ሁሉንም አካላት ማሳተፍ ነው። በርግጥ ምርጫ ቦርድ ያለበትን አድሎ ቀርፎ፣ ለማንም ወገንተኛ ባልሆኑና ልምዱና የትምህርት ዝግጅቱ ባላቸው ሰዎች ቢመራ አንድ ነገር ነው። ነገር ግን የፖሊስ እና ደኅንነት አካላት (ከሥልጣን ያዥው ውጪ ያሉት) ተወዳዳሪ ፓርቲዎች እና መራጮችን ማዋከብ ማቆም አለባቸው። የተሰደዱ ፖለቲከኞች እና የፖለቲካ ድርጅቶችም ተስፋ አስቆርጦ ያሰደዳቸው እና ነፍጥ ያስነሳቸው መንስዔ ተቀርፎ ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ዋስትና መስጠት የግድ ነው። ይህንን ለማድረግ በአንድ ወገን “ሁሉን ዐቀፍ ድርድር መደረግ አለበት” የሚል ሙግት አለ። የዚህ ሙግት ዋነኛ አራማጅ በቅርቡ ከእስር የተፈታው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ነው። በሌላ በኩል “ድርድሩ የግድ አያስፈልግም” የሚሉም ወገኖች አሉ። ለምሳሌ ፖለቲከኛው ግርማ ሰይፉ ጋር በአንድ ጫወታችን መሐል ‘ተቃዋሚው ከኢሕአዴግ ጋር የግድ መደራደር የለበትም። ኢሕአዴግ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን ተወጥቶ ለነጻ ውድድር የምርጫ ሜዳውን በሐቅ ካመቻቸለት ከዚያ በኋላ ያለው የተቃዋሚው ሥራ ነው’። እርግጥ አሁን ከውስጥም ከውጭም ያለው ግፊት ከፊል ፍሬ አፍርቶ፣ “ለውጥ አይመጣም” ከሚል ድፍንፍን ያለ ግዜ “ምን ዓይነት ለውጥ ይመጣ ይሆን?” ወደሚል ጉጉት ተሸጋግረናል። ይህንን የለውጥ ተስፋ ወደ ተግባር እንዲለወጥ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ብዙ ይጠበቃል። 
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ባለው የተዝናና ሁኔታ ለቀጣዩ ምርጫ አገሪቷን ቢያዘጋጁ አገር ውስጥ ያሉ ተቃዋሚዎች አፈር ከላሱበት ተነስተው በውስጣዊ ወጀብ የሚሰቃየውን ኢሕአዴግ መፈተናቸው አይቀሬ ነው። ፈተናው ኢሕአዴግን ወደለመደው ጫወታ የመመለስ ዕድሉም እንዲሁ ሰፊ ነው። ምናልባት አቶ ዐብይ አሕመድ፣ አቶ ለማ መገርሳና ጥቂት የለውጥ ፊቶች በምርጫ ክልላቸው በብልጫ ያሸንፉ ይሆናል። ነገር ግን በሌሎቹ የምርጫ ክልሎች ውስጥ ሕዝቡ ላይ ግፍ ሲያደርሱ የነበሩ የኦሕዴድ ካድሬዎች ለሕዝቡ ጥቅም ሲታሰሩ ሲፈቱ የከረሙትን የኦፌኮ አባላትን አያሸንፉም። ከኦሮምያ ውጪም ተመሳሳይ ሁኔታ ይኖራል። ኢሕአዴግ ይህን ፈታኝ ሁኔታ በተለመደው የማዋከብ፣ የማሳደድ እና የማሰር ስልት ለመጋፈጥ የሞከረ ዕለት ደግሞ የተካበው ተስፋ ሁሉ ይናዳል። ጫወታው ፈረሰ፤ ዳቦው ተቆረሰ!
በአንድ ወቅት ከሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ አሰፋ ጋር ቃለ ምልልስ ሳደርግ፣ “ኢትዮጵያን የሚያተራምሳት ዴሞክራሲ ማጣት አይደለም፤ የዴሞክራሲ ተስፋ ማጣት ነው” ብሎኝ ነበር። እውነትም የዛሬውን አገራዊ መረጋጋት ስንመለከተው በተስፋ ላይ የቆመ መረጋጋት ነው። የዚህ ተስፋ መፍረስ፣ የሚያፈርሰው ብዙ ነገር ነው። 
በሥልጣን መጫወት፣ በእሳት መጫወት!
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሐቀኛ የለውጥ ፍላጎት ካላቸው፣ ‘ይህ በኔ ዘመን አይከሰትም’ ብለው ሊያስቡ ይችላሉ። ይህ ግን የሰውን ራስ ወዳድ ተፈጥሮ እንዲሁም የሥልጣንን አባላጊነት ካለመረዳት የሚመነጭ ነው። ብዙዎቹ የዓለማችን አምባገነኖች በአንድ ወቅት ሐቀኛ የለውጥ አርበኞች ነበሩ። አንዴ የሥልጣን መደላደል ከፈጠሩ በኋላ ግን በምናባቸው በሚፈጥሩት “የለውጡ ጠባቂነት” ሚናቸው ተሸፍነው ከቀዳሚዎቻቸው የበለጠ ጉዳት ያደርሳሉ። ብዙዎቹ የለውጥ አርበኞች የመጣው ለውጥ እንዳይቀለበስ በሚል ሰበብ አስባብ ለረዥም ግዜ ሥልጣን ላይ ይከርማሉ፣ የሚያምኗቸውን ሰዎች ብቻ መርጠው ቁልፍ ቦታ ላይ ይሾማሉ፣ የለውጥ ሒደታቸውን የተቃወሙትን ‘አድኀሪያን’ በፈርጣማ ጡንቻዎቻቸው ይጨፈልቃሉ፣ በመጨረሻም ‘ለውጥ’ የሚሉት የራሳቸውን ሥልጣን ተቆናጦ መቆየት ብቻ እስኪመስል ድረስ ፈላጭ ቆራጭ ይሆናሉ – በአጭሩ አምባገነን ይሆናሉ። ከለውጥ አምጪነት፣ መለወጥ ያለበት አካል ወደ መሆን ይሸጋገራሉ። 
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ለውጪያዊ መረጋጋት እና ለውስጣዊ መስማማት ግዜ ባገኙ ቁጥር፣ ሰው ናቸውና በሥልጣን የመበላሸት ዕድላቸውም ሰፊ ነው የሚሆነው። የሥልጣን መደላደል “ከእኔ ወዲያ ላሳር” ወደሚል ትምክህት ይመራቸዋል። ስለዚህ ከላይ “አሁን ያለው የተዝናና ሁኔታ” ያልኩት በእርሳቸው ይሁንታ ብቻ የመጣው መልካም ጊዜ ለፈተና ግዜ አይፀናም። ሹመኞች በጭንቅ ግዜ የማይገቡት ቃል የለም። ዕውቁ ፖለቲከኛ አንዷ-ዓለም አራጌ “we are victims of broken promises” (‘እኛ የተከዱ ቃልኪዳኖች ሰለባ ነን’) ያለው በጭንቅ ግዜ የተገቡ ቃል ኪዳኖች፣ በመረጋጋት ግዜ ስለሚዘነጉ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለገቧቸው ቃልኪዳኖች ማስተማመኛ አስቸኳይ ሕጋዊ ዋስትና ይስጡ። የሚሻሩት ዐዋጆች አሁኑኑ ይሻሩ፣ የሚሻሻሉት ዐዋጆች አሁኑኑ ይሻሻሉ፣ የሚጨመሩት ድንጋጌዎች አሁኑኑ ይጨመሩ… የተቋማት ገለልተኝነት ሥራ መሠረቶች አሁኑኑ ይጣሉ… ለቀጣዩ ምርጫ ያለው መሰናዶ በሕግ እና ተቋማዊ አግባብ በአስቸኳይ ይፈፀሙ። የፖለቲካ ዕርቅ ጥሪዎች በነቢብ ሳይሆን በገቢር ይደረጉ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እነዚህን ነገሮች በማለዳ ማድረግ ከቻሉ ብዙዎቹ ለውጥ-ፈላጊ የዓለማችን ሰዎች ከወደቁበት ገደል ይተርፋሉ። ሥማቸውም “ከአብዮት ከዳተኞች” ተርታ ሳይሆን፣ ምናልባትም ከዘመን ባንዴ ብቻ ከተከሰቱት “ከጨቋኞች መሐል የወጡ የነጻነት ፋና ወጊዎች” – ከእነ ፍሬድሪክ ደ ክላርክ ተርታ ይመደባሉ። ምርጫው የእርሳቸው ነው፤ ራስን ከራስ ማዳን ወይም በሥልጣን መጫወት።

(ይህ ጽሑፍ በ1992 ከታተመው “Ethnic Federalism in a Dominant Party State: The Ethiopian Experience 1991-2000” ከሚለው የሎቪስ አለን ጥናት ውስጥ ካለ ንዑስ ርዕስ ተቀንጭቦ የተተረጎመ ነው።)
በሽግግር መንግሥቱ ግዜ የታተሙት ዐዋጆች ሁሉ ክልሎች እና ንዑስ ክፍሎቻቸው የማዕከላዊ መንግሥቱ ምንዝሮች እንደሆኑ ተመልክቷል። የሽግግር ምክርቤቱ ለብሔሮች ‹የራስን ዕድል በራስ መወሰን› የሚል ቃል በስተቀር የክልሎች ሥልጣን የተገደበ ነበር። የኢትዮጵያ መንግሥት ያልተማከለ፣ አሀዳዊ፣ ወይም ፌዴራላዊ ስለመሆኑ ምንም አይታወቅም ነበር። የ1987ቱ ሕገ መንግሥት ግን ይህንን ግራ መጋባት ቀርፎታል። አሀዳዊውን ስርዓት በመተው ፌዴራላዊውን እንደሚከተል በግልጽ ያስቀምጣል (አንቀፅ1)። ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ የፌዴራል አወቃቀር ላይ በርካታ እንግዳ እና አሻሚ ነገሮች አሉ። ይህም ከነባር ፌዴሬሽኖች የፌዴራል ኅልዮት እና አተገባበር አንፃር ይገጥማሉ ወይም ይጋጫሉ የሚለውን የመደምደሙን ነገር  ከባድ ያደርገዋል። የመገንጠል መብት፣ ለፌዴሬሽኑ አባል አገረ-መንግሥታት ፈንታ ሉዓላዊነት “ለብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች”  መሰጠቱ፣ ገለልተኛ የሕገ መንግሥት ፍርድ ቤት አለመኖር፣ እና ጠንካራው የሥራ አስፈጻሚ አካል ለዚህ ውስብስብ ባሕሪው ተጨማሪ ምክንያቶች ናቸው።
የክልሎች ሥልጣን ተቃርኖ
በኢትዮጵያ ፌዴራል አወቃቀር ግልጽ የሆነ አያዎ እንዳለ ብዙ ጸሐፊዎች አስፍረዋል። በአንድ በኩል ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች የተወሰኑ ሁኔታዎችን አሟልተው የመገንጠል መብት ተሰጥቷቸዋል። ይህ ከሌሎች የፌዴራል ስርዓታት በተለየ የፌዴራሉ አካላትን ነጻነት የተለጠጠ ያደርገዋል። በሌላ በኩል፣ የአባል አገረ-መንግሥታቱ ሥልጣን በአንፃሩ በጣም ውሱን ነው። የክልል መንግሥታቱ ሥራቸውን ለመሥራት በፌዴራል መንግሥቱ ላይ ጥገኛ ናቸው። በብሬዝኬ እንደተገለጸው፣ ሕገ መንግሥቱ “ጥቂት የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብቶችን መድኅን” ያቀርብና፣ እስከ መገንጠል በሚለው መካከል ምን እንዳለ ስላልተገለጸ፣ ጠባብ የራስን ዕድል የመወሰን ቅርፅ እና የተገደበ የባሕል ነጻነት ያጎናፅፋል።”
ዱካቼክን ጨምሮ የተወሰኑ የፌዴራሊዝም አጥኚዎች የመገንጠል መብት አንድን አገረ መንግሥት ፌዴራላዊ ለመባል እንዳይበቃ ያደርገዋል በማለት እስከመከራከር ይደርሳሉ። የመገንጠል መብት ዜጎች ለማዕከላዊ መንግሥቱ ያላቸው ታማኝነት ቀስ በቀስ እንዲቀንስ ያደርገዋል። በተጨማሪም፣ ክልሎች ኅብረቱን የመልቀቅ ነጻነቱ ሲኖራቸው፣ በማዕከሉ እና አገረ መንግሥታቱ መካከል ያለው የፖለቲካ መዋቅር ከፌዴሬሽን ይልቅ የላላ ንዑስ ብሔራዊ ቁጥጥር ያለው ኮንፌዴሬሽን ዓይነት ይሆናል። ሉዓላዊነት ለብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች መሰጠቱም ቢሆን ብሔረሰቦች ከፌዴሬሽኑ ብቻ ሳይሆን ከክልሉ አገረ መንግሥታት ሳይቀር እንዲገነጠሉ ሊያደርግ ይችላል። ይህ ያልተለመደ ሕገ መንግሥታዊ ስርዓት ከመሆኑም ባሻገር የሚመስለው አንድም የፌዴራል ስርዓት ዛሬ ላይ የለም። የመገንጠል መብት መኖር ኢትዮጵያን ፌዴራላዊ ለመባል አያበቃትም የሚለው እንደ አስተያየት ሰጪው ይወሰናል። ሌሎች የፌዴራል ስርዓቶችን ብንመለከት፣ አንዳንድ የዘውግ ቡድኖችን ወይም ክልሎችን የመገንጠል መብት የሰጡ ስርዓቶች አሉ። ነገር ግን እነዚህኞች ከሕገ መንግሥት ድንጋጌዎች ውጪ የተሰጡ ናቸው።
እንደስፔንና ካናዳ ያሉ ኅብረብሔራዊ ፌዴሬሽኖች መሰል ፈቃዶችን በዘውግ ለተለዩ ክልሎች ሰጥተዋል። ሆኖም እነዚህ ፈቃዶች ከሕገ መንግሥት ውጪ ነው የተደነገጉት። ይህም መዋቅሩን የበለጠ ተለዋዋጭ አድርጎታል። ይህንንም ማድረግ የተቻለው ቀስ በቀስ የወቅታዊ የፖለቲካ ፍላጎቶችን ለማሟላት ነው። ኩዩቤክ ውስጥ ያሉ የፖለቲካ ኃይሎች ከካናዳ ፌዴሬሽን ለመገንጠል እንቅስቃሴ ሲጀምሩ፣ በካናዳ የፖለቲካ ሒደት ውስጥ ሕገ መንግሥቱን ማሻሻል ሳያስፈልግ ትልቅ ለውጥ ተደርጓል። የኪዩቤክ ገዢ ፓርቲ በሪፈረንደም ከተሳካለት ሉዓላዊ አገር የመፍጠር መብቱን አረጋግጧል። እኤአ የ1995ቱ የሉዓላዊነት ዐዋጅ የዚያን ዓመት የተካሔደውን ሪፈረንደም ማሸነፍ ቢችሉ ኖሮ ለኪዩቤኮች የመገንጠል ሕጋዊ ዕድል ሰጥቷቸው ነበር። 
የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ከስፔኑ የ1978 (እኤአ) ሕገ መንግሥት ጋር ሊነፃፀር ይችላል። ልክ እንደ ኢትዮጵያ ስፔን ደም አፋሳሽ የመንገንጠል ንቅናቄ እና ዴሞክራሲያዊ ያልሆነ ታሪክ ችግር ነበረባት። እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ፣ የስፔን መንግሥት የሆነ ዓይነት ነጻነት ማስተዋወቅ ፈልጓል። ነገር ግን ክልሎቹን እና የጥያቄ አቅራቢዎቹን ድንበሮች በሕገ መንግሥታዊ አንቀፆች ለመለየት አልሞከረም። በምትኩ፣ “ራስ ገዝ ማኅበረሰቦች” በሚል ቀስ በቀስ የሚያድግ ራስን የማስተዳደር ሥልጣን ተሰጣቸው። ይህም የሆነው በሌሎች የፌዴራል መንግሥታት ከተለመደው በተለየ ሁኔታ በክልል እና ማዕከላዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር ነበር። ሆኖም፣ ዋናዎቹ የመከላከያ እና የኢኮኖሚ አውታሮች በማዕከላዊው መንግሥት ቁጥጥር ሥር ናቸው። ራስ ገዝ ማኅበረሰቦቹ ሁሉም እንደየ ድርድራቸው የተለየ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት ነው የተሰጣቸው። ይህ አለመመጣጠን ከአዲሱ የራሽያ ፌዴሬሽን ጋር አንዳንድ መመሳል አለው። በ1992ቱ (እኤአ) የራሽያ ፌዴሬሽን ስምምነት የተለያዩ የዘውግ ሪፐብሊኮች የመገንጠል መብት ተሰጥቷቸው ነበር። ይህ የሶቪየት ኅብረት ግዜም የነበረ ነው። ሆኖም ስምምነቱ (እኤአ) በ1993 ሲከለስ ተሰርዟል። በፈንታው፣ ማዕከላዊው መንግሥት ከዘውግ ሪፐብሊኮቹ ጋር ሥልጣን የመጋራት የሁለትዮሽ ስምምነቶችን መደራደር የጀመረበት “ድኅረ ሕገ መንግሥታዊ ሒደት” ውስጥ ገብቷል። 
የካናዳ፣ ስፔን እና ራሽያ ሕገ መንግሥቶች የመገንጠል መብትን አላካተቱም። ነገር ግን በተግባር የተለጠጠ “የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መድኅኖችን” ለአባላቱ የተለያየ የራስ ገዝ አስተዳደር ሰጥተዋል። የኢትዮጵያ ፌዴሬሽን ግን በተቃራኒው መሔድን መርጧል። የመጨረሻውን የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት ማለትም የመገንጠል መብትን ሰጥቶ የክልሎቹን የለት ጉዳዮች ለመፈፀም የሚያስፈልገውን ሥልጣን ግን ባንፃሩ ይገድበዋል። መሬት እና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች ለምሳሌ የሚተዳደሩት በፌዴራል ሕግጋት ነው። የክልል መንግሥታቱ የዕለት ተለት ሥራቸውን ለመከወን የአገርዐቀፉን መደብ መከተል አለባቸው። ይህም ማለት በፌዴራሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚፀድቀው የአምስት ዓመት የኢሕአዴግ ዕቅድ በሁሉም የክልል መንግሥታት፣ በያንዳንዱ የአስተዳደር እርከን ተፈፃሚ መሆን አለበት። የክልል የገቢ ምንጮች ከፌዴራሉ አንፃር ጥቂት እና እዚህ ግባ የማይባሉ ናቸው። ይህም ማለት የክልል መንግሥታት ሥራዎቻቸውን ለመከወን የፌዴራል መንግሥቱ ድጎማ እና ሥጦታ ላይ ጥገኛ መሆን አለባቸው። 
ቁጥጥር አልባው ገዢ ፓርቲ 
በርካታ የፌዴራሊዝም አጥኚዎች እንደሚሉት አንድ ፌዴሬሽን መንግሥት ከሕግ በታች ካልሆነ ሐቀኛ ሊሆን አይችልም፡፡ የፖለቲካ ኃይሎቹ በሕገ መንግሥቱ የተቀመጡትን ድንጋጌዎች ካላከበሩ የተሰጡት ዋስትናዎች ዋጋ የላቸውም፡፡ መንግሥት ለሕግ ታዛዥ መሆኑን ለማረጋገጥ የፌዴራል ስርዓቱን አተገባበር እና የፖለቲካ አመራሮችን ሥራዎች መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን የሕግ ማዕቀፉ በራሱ የፌዴራል ስርዓቱ የፌዴራል እና ክልሎች ግንኙነትን በመወሰን ረገድ መዋቅራዊ የቁጥጥር ድንጋጌዎችን መጣል አለበት፡፡ እዚህ ጋር መነሳት ያለበት ጥያቄ ‹የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት የፖለቲካ አመራሩ የፌዴራል መርሖችን እንዳይጥስ በቂ የቁጥጥር መንገዶችን አስቀምጧል ወይ?› የሚለው ነው፡፡
እንደ አሜሪካው ዓይነት የፌዴራል ስርዓት ውስጥ፣ የሕግ አውጪው ሁለተኛ ምክር ቤት የሌሎች የፌዴራል ተቋማትን ሥልጣን በመቆጣጠር የሥልጣን ክፍፍልን በተመለከተ መሠረታዊ ሚና ይጫወታል፡፡ እንደ አውስትራሊያ እና ካናዳ ባሉ የፓርላሜንታዊ ፌዴራል ስርዓቶች ውስጥ ደግሞ ሁለተኛው ምክር ቤት የአገርዐቀፉ መንግሥት ሕጋዊ ተግባራት ውስጥ ክልሎቹ መማከራቸውን ያረጋግጣል፡፡ በኢትዮጵያ ሁለተኛው ምክር ቤት፣ ማለትም የፌዴሬሽን ምክር ቤቱ አንዳቸውንም መሰል ዓይነቶቹን ክፍተቶች አይሞላም፡፡ የኢትዮጵያ ስርዓት በተፈጥሮው ፓርላሜንታዊ ነው፤ ነገር ግን የፕሬዘዳንታዊ ስርዓት ፀባይ አለው፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት እና በአፅፈፃሚው አካል መካከል ያለው ግንኙነት የሚዳኘው በምክር ቤቱ መርሕ መሆኑ በአሜሪካ ሕገ መንግሥት እንደሚታየው ዓይነት የሥልጣን ክፍፍልን እና የቁጥጥር መንገዶችን ይቀንሳል፡፡ ነገር ግን ከሌሎች የፓርላሜንታዊ ስርዓቶች በተለየ ሠራዊቱ እና የምኒስትሮች ምክር ቤት ተጠሪነታቸው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትልቅ ሥልጣን አለው፡፡ በተጨማሪም፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤቱ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን በሕግ ማውጣት ሒደት ውስጥ የሚቆጣጠርበት መንገድ የለውም፡፡ ይህም ከሌሎች ባለሁለት ምክር ቤት ስርዓቶች አሠራር ጋር ይቃረናል፡፡ ከላይ እንደተገለጸው፣ ሕገ መንግሥቱ አደጋ ላይ በሆነ ግዜ ብቻ ነው የፌዴሬሽን ምክር ቤቱ ጣልቃ ገብቶ ውሳኔ የሚያሳልፈው፡፡ በዚህም ክልሎች በፌዴሬሽን ምክር ቤቱ በኩል ጠቅላላ የፌዴራል ድንጋጌዎችን የመምከር ወይም በፌዴራል ደረጃ ሕግጋትን የመጠቆም ምንም ዕድል የላቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴሬሽን ተቋማዊ መዋቅር ለተጠናከረ ማዕከላዊ የሥራ አስፈፃሚ አካል ቦታ የሚሰጥ ሲሆን የፌዴሬሽኑም ይሁን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱ ማዕከላዊ የሥራ አስፈፃሚውን ለመቆጣጠር የሚያስችለው ተቋማዊ ሁኔታ አናሳ ነው፡፡
በብዙዎቹ የፌዴራል ስርዓቶች ውስጥ፣ ነጻ የሕገ መንግሥት ፍርድ ቤት ስላለ ሕገ መንግሥቱን የመተርጎም እና ተለዋዋጭ ኩነቶች ጋር የማስማማት ሥራዎችን ያከናውናል፡፡ ገለልተኝነቱ የግድ አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም የፖለቲካ ኃይሎች እና ሁሉም የአገሪቱ ወገኖች ለማንም እንደማያደላ አውቀው ውሳኔውን እንዲቀበሉ ያደርጋል፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራል ስርዓት  የሕገ መንግሥት ፍርድ ቤት ስለሌለው ከሌሎቹ ስርዓቶች ይለያል፡፡ በምትኩ፣ ሕገ መንግሥታዊው ጉዳይ ለፖለቲካው አካል፣ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ ተትቷል (አንቀፅ 62)፡፡ በፍርድ ቤት የሚነሳ ማንኛውም አለመግባባት የሚታየው በፌዴሬሽን ምክር ቤት ሥር በ1988 በተቋቋመው የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔ ነው፡፡ ጉባዔው የተቋቋመው ከፖለቲካ እና የሕግ አካላት ተውጣጥቶ ነው፡- እነዚህም የፍርድ ቤቱ ፕሬዚደንት እና ምክትላቸው፣ ሦስት የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት እና በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተመረጡ ስድስት የሕግ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ጉባዔውም በመጨረሻ ለፌዴሬሽን ምክር ቤቱ ጥቆማውን በመላክ ውሳኔ ያስገኝለታል (አንቀጥ 83)፡፡
ይህ የሚያመለክተው የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ፈጣሪዎች በክልሎች መሐል የሚነሱ አለመግባባቶች በሕግ አግባብ ይፈታሉ ብለው የማያምኑ መሆኑን፣ ነገር ግን የሆነ ዓይነት ፖለቲካዊ መፍትሔ መኖር አለበት ብለው መገመታቸውን ነው፡፡ ይሁን እንጂ በተግባር፣ ምንም እንኳን ፍርድ ቤቶች በጥቅሉ ነጻ ቢሆኑም፣ የሕገ መንግሥት ትርጉም ሥራ ሥልጣን በተቆጣጠረው የፖለቲካ ፓርቲ እጅ ነው፡፡ የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔ አባላትን ጨምሮ ዳኞች የሚሾሙት በጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ነው (አንቀፅ 81)፡፡ ነጻ የሕገ መንግሥት ፍርድ ቤት አለመኖሩ፣ የኢትዮጵያ ስርዓት መንግሥታዊ የሥልጣን ገደቦች ስለሚያጥሩት ለሕገ መንግሥታዊነት መርሖች ቁርጠኝነት እንዳይኖር ማድረጉን እንዲናገሩ ታዛቢዎችን አስገድዷቸዋል፡፡ ነገር ግን፣ ለምሳሌ፣ የኢትዮጵያን ስርዓተ ናሙና ከራሽያ ፌዴሬሽን ጋር ካወዳደርነው የኢትዮጵያ ስርዓት ቁጥጥር ማጣት በአንፃሩ የተሻለ ነው፡፡ የራሽያ ሕገ መንግሥት ለፕሬዚዳንቱ የሕግ ክለሳ እና በክልሎች እና በፌዴራል መንግሥቱ መካከል ያሉ አለመግባባቶችን የመገላገል ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ይህም ከፌዴራላዊ መርሖች ያፈነገጠ ነው፤ የማዕከሉ ባለሥልጣናት ለብቻቸው የፌዴራሉ አባላትን ሥልጣን መወሰን የለባቸውም፡፡ 

ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ የዛሬ 8 ዓመት ገደማ፣ በመስከረም ወር 2003ቱ የኢሕአዴግ ጉባዔ ላይ ተገኝቶ ንግግር አድርጎ ነበር። እናም “እናንተ ፖለቲካውን ሥሩ፣ ንግዱን ለኛ ተዉልን” የሚል ንግግር አድርጓል። ንግዱን አልተዉለትም። ሆኖም ምንጩ በሚታወቀው ሀብቱ እየተፎካከራቸው ነው። እነርሱ በወቅቱ የፈለጉት በሕዝቡ የሚወደደውን ሰው ወደ መድረካቸው በማምጣት ከሕዝባዊ መውደዱ መሻማት/መፎካከር ነበር። ከዚያ ቀጥሎ ለመጀመሪያ ግዜ ክብረወሰን ሲሰብር የለበሰውን ቲሸርት ለወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በሥጦታ አበረከተላቸው። መብቱ ነው ግን ይህም አልበቃው፣ በአትሌቲክስ ሜዳ ክብረወሰን ሲሰብር ከተሰማው ደስታ ይልቅ እዚያ መድረክ ላይ በመገኘቱ የተሰማው ደስታ እንደሚበልጥ ተናገረ። ይሁን። ዞሮ ዞሮ ግን ኃይሌ ለዚህ ሙገሳው በምላሹ የጠየቀው ‘ውለታ’ “ንግዱን ተዉልን” የሚል ብቻ ነበር። በርግጥ ከዚያ በፊት “የአገር መሪነት ማን ይጠላል?” የሚል ቃል ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፤ የግንባሩ አባል ቢሆን የሆነ የአመራር ቦታ የሚከለክሉት አይመስለኝም። ሆኖም ከዚያ በፊት የነበረው የፖለቲካ ልምድ ግን የቅንጅት አመራሮችን በሽምግልና ሥም ይቅርታ ያስፈረመው የአገር ሽማግሌዎች አባልነት ብቻ ነበር። 
ኃይሌ ገብረሥላሴን በመተቸት ለመጻፍ ስንጀምር “ኃይሌ ለአገር ውለታ የዋለ፣ ከአትሌቲክስ ጡረታ ቢወጣም በኢኮኖሚው መስክ ብዙ ሰው ለመቅጠር የበቁ ኢንቨስትመንቶች ላይ የተሠማራ” የሚሉ ማባበያዎችን ማስቀመጥ እንደ ደንብ ተቆጥሯል። እኔ ይህን አላደርግም። ለትችት የሚቀርቡት ሰዎች ስለአገር ምንም ውለታ ያልዋሉ ሰዎች ናቸው ማለት አይደለም። ሁሉም የአቅሙን አዋጥቷል። ኃይሌም ቢሆን በፍትሕ ዓይን ከማንም አይበልጥም። አሁን በኢትዮጵያ ያለው ተቃውሞ ደግሞ የፍትሓዊነት ጥያቄ ነው። የፍትሓዊ አስተዳደር፣ የፍትሓዊ ውክልና፣ የፍትሓዊ የሀብት ክፍፍል፣ የፍትሓዊ ዳኝነት፣ ወዘተ።
ከሁለት ዓመት በፊተ፣ በሕዳር ወር 2008 ቢቢሲ ሬድዮ ላይ ቀርቦ የነበረው ኃይሌ “ዴሞክራሲ ለአፍሪካውያን ቅንጦት ነው” ብሏል። ‘ዳቦ ይቅደም’ ማለቱ ነው። ሆዱን ያልሞላ ሰው ነጻነት አያስፈልገውም ከሚለው “የባርነት ለዳቦ” አስተሳሰብ ጋር የተስተካከለ አባባል ነው። አንድም በድሃ መሳለቅ ሲሆን፣ አንድም ደግሞ በዘር መፈረጅ ነው። ኃይሌ ለመናገር ያለው ድፍረት መልካም ነበር። የሚያሳዝነው ለሚናገረው ነገር ይዘት እና ውጤት ቅንጣት አለመጨነቁ ነው። ብዙ ሰዎች በሱ ንግግር የሚበሳጩት ካለው ሕዝባዊ ተቀባይነት አንፃር ንግግሩ ተፅዕኖ ስለሚያሳድር ነው። ‘ከነጻነት ዳቦ ይቀድማል’ የሚል መልዕክት ያለው ንግግር ሲያደርግ፣ ለሕዝቡ ጭቆናውን ለልማት ሲባል ቻሉት ማለቱ ነው፤ ለመንግሥቱ ደግሞ ሕዝባችሁን ዳቦ እየሰጣችሁ፣ ብትረግጧቸው ምንም አይለይም እያለ ነው። ነገሩ ከዘረኛ ነጮች አመለካከት ጋርም ይሠምራል። ለቅኝ አገዛዝ የተሰጠው አስተያየት (ማብራሪያ) ተመሳሳይ ነው። አፍሪካውያን ድህነት ይዘው እንጂ የምዕራባውያኑን ልብስ ቢያጌጡበት ያምርባቸዋል። የተመጣጠነ ምግብ ቢበሉ ይስማማቸዋል። እንደ ሕዝብ ሉዓላዊነታቸው ቢከበርላቸው ደስ ይላቸዋል። አፍሪካዊ ስለሆኑ የቅንጦት አይሆንባቸውም። ልማትና ዴሞክራሲም የሚጣረሱ ነገሮች አይደሉም። ሁለቱንም ባንዴ ማቅረብ ይቻላል። አፍሪካውያንም እንደሌላው ሁለቱንም ባንዴ ቢያገኙ አይጠሉም።
ከሰሞኑም በድጋሚ ኃይሌ አወዛጋቢ መልዕክቱን በድጋሚ አስተላልፏል። በኢቢሲ ከፓስተር ዳንኤል ጋር ቀርቦ የተናገረው ንግግር ውስጥ የሚያስቆጣ ይዘት ያላቸው ንግግሮች ደንቅሯል። ለምሳሌ “የውጭ እንትን ያለበት… የሚታይበት ነገር” በማለት የገለጸው እና በኋላ ሲተነትነው የግብጽ ስፖንሰርነት አለበት ለማለት እንደፈለገ የሚያስታውቀው ንግግሩ አንዱ ነው። ኢትዮጵያውያን በቂ ብሶት የሌላቸው ይመስል የመንግሥትን ፕሮፓጋንዳ ሰምቶ የውጭ ተልዕኮ አስፈፃሚዎች ሥራ ማስመሰል ተገቢ አይደለም። የውጪ ኃይሎች ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ተቃውሞ ሊደግፉ ይችላሉ እንጂ ሊፈጥሩት አይችሉም። አለቀ። 
ሲቀጥል ደግሞ “ቤት በመዝጋት፣ ትራንስፖርት በመዝጋት” መቃወም “የትም አገር የሌለ” ነገር ነው። ብሎ አጣጥሎታል። በመሠረቱ ኃይሌ ብዙ አገራት መሔዱ እውነት ነው። ነገር በሔደባቸው አገሮች ውስጥ ያለውን የፖለቲካ ስርዓት፣ ለተቃዋሚዎች ተሳትፎ የሚሰጡትን ቦታ እና የሕዝብን ጥያቄ የሚያስተናግዱበትን መንገድ ያጠና ወይም ለማጥናት ግዜ ያገኘ አይመስለኝም። 
ሕዝቦች ወይም የሕዝብ ክፍሎች ጥያቄ ወይም ቅሬታ ሲኖራቸው፣ ሲያሻቸው በመሾምና በመሻር፣ ሲያሻቸው ፖሊሲ በማስወጣት እና በማስከለስ የሚኖሩበት ዘመን ላይ ነን። የኛው መንግሥት ደግሞ መጀመሪያ በነፍጥ ራሱን ሾመ፣ በመቀጠል ፍትሓዊ ባልሆኑ የምርጫ ሒደቶች ሥልጣኑን አስቀጠለ። የሕዝብ ወኪል ማኅበራትን እና ሚድያዎችን አደከመ። በዚህ መንገድ ተናጋሪ እራሱ፣ ፖሊሲ ቀራጭ እራሱ፣ ሁሉ ነገር ራሱ ከመሆኑ የተነሳ የተቃውሞ መንስዔዎቻችሁን ሳይቀር እኔ ራሴ ነኝ የምነግራችሁ አለ። ሕዝቦች በድርጅት የጀመሩትን ተቃውሞ አደናቀፈ። ድርጅቶች ፈርሰውና ተዳክመው ዜጎች በየፊናቸው መቃወም ቀጠሉ። 
ኃይሌ የተቃወመው የሠላማዊ ትግል መንገዶችን ነው። በመሠረቱ በሠላማዊ ትግል ሦስት ደረጃዎች አሉ። የመጀመሪያው ማግባባት ነው፤ በጽሑፍ፣ በሠልፍ… ብዙ ተሞክሮ ሰሚ አልተገኘም። ሁለተኛው፣ አለመተባበር ነው፤ መንግሥት መር ጥፋቶች ሲፈፀሙ የነዚያ ተግባራት አካል ላለመሆን ብዙ ተሞክሯል፣ እየተሞከረም ነው። ግን ሦስተኛውም ተጀምሯል። ጣልቃ መግባት፤ መንግሥት ለጥያቄዎች መልስ አልሰጥም ሲል እና ችግሮች ከድጡ ወደማጡ እየገቡ ሲያስቸግሩ ጣልቃ ገብቶ ይበቃል እንደማለት። ይህ ደረጃ ችግሩ እነርሱን ስለማይነካቸው ብቻ ሠላማዊ ትግሉን የሚቃወሙት ሰዎች የችግሩ ጥልቀት ባይገባቸውም ጫፍ ጫፉ እንዲታያቸው ማድረግ ነው። ችግሩ ከማይገባቸው ሰዎች መካከል የናጠጡ ሀብታሞች ይገኙበታል። 
በመሠረቱ የኃይሌ ችግር የብቻው አይደለም። የሙለር ሪል ኢስቴት ባለቤት አቶ ሙሉጌታ ተስፋኪሮስ ከአንድ ታዋቂ የጀርመን ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ “ኢትዮጵያ ለዴሞክራሲ ዝግጁ አይደለችም” ብለዋል። የሚገባቸው መልስ ከላይ ለኃይሌ ከተሰጠው የተለየ ሊሆን አይችልም። ጥያቄው ‘ሀብታሞችን ከሕዝባዊ ተቃውሞዎች ተፃራሪ የሚያቆማቸው ምንድን ነው?’ የሚል ነው። 
ለመልሱ ደጋግሜ ወደጠቀስኩት የአሴሞግሉ እና ሮቢንሰን ‘Economic Origin of Democracy and Dictatorship’ የሚል መጽሐፍ ላይ ያገኘሁት ኅልዮትን ልዋስ። የኢኮኖሚ ልኂቃን ሁሌም የአምባገነንነት ደጋፊዎች ናቸው። የሀብት ክፍፍል በሰፋ ቁጥር ሕዝቦች ያምፃሉ። ይህ ዴሞክራሲ በግዚያዊነት ለውጥ ሊያመጣ ይችላል። ነገር ግን አሁንም የኢኮኖሚ ልኂቃኑ የመንግሥት ግልበጣ ደግፈው በኢኮኖሚ የብቻ የበላይ የሚያደርጋቸውን አምባገነናዊ ስርዓት ያቆማሉ። ማለትም ከድሀው ብዙኃን እጅግ የራቀ ሀብት ያላቸው ባለፀጎች ባሉበት አገር ዴሞክራሲ አይፈጠርም፤ ቢፈጠርም አይፀናም። ኃይሌ ገ/ሥላሴ እና ሌሎቹም ባለፀጎች ኢትዮጵያ እና አፍሪካ ለዴሞክራሲ እንዳልተዘጋጁ የሚናገሩት ወይም እንዳይዘጋጁ የሚፈልጉት የኢኮኖሚ ልኂቅነት ጥቅማቸውን (privileges) ለማካፈል ስለሚቸግራቸው ነው። 
አሁን ኃይሌ በይፋ ፖለቲከኛ መሆን እንደሚፈልግ እየተናገረ ነው። ፖለቲከኝነት የሕዝብን ውክልና አግኝቶ ጥቅማቸውን ለማስከበር የሚሠራበት መሆኑን ተረድቶ፣ ይህን የኢኮኖሚ ልኂቅነት ቦታውን እስከመታገል መድረስ መቻል እንዳለበት ከአሁኑ በይፋ ያስብበት ዘንድ ጊዜው አሁን ነው። 

On 11th of October 2017, the State-run Ethiopian Human Rights Commission (EHRC) has written the long awaited report of its investigation of rights violation against Qilinto Fire defendants as per the request of the 19th Bench of Federal High Court at Lideta. On the five pages of report, EHRC revealed scars left after tortures during investigation against 16 defendants among 38 people charged under the same case. The report also revealed flogging marks left on the defendants’ backs, breaking of fingers, scars left after nail-pierced body parts and uprooted finger nails of multiple defendants. Here below I will jot down the torture scars listed in the report and will follow what the defendants have written in response:

  1. Kebede Chemeda – a scar on his right hand; breaking in his right hand thumb
  2. Ibrahim Khamil – a scar on his right leg; a scar on his left hand; scar-marked left from handcuffs
  3. Agbaw Setegn – large scar on his left leg thigh; a scar on his right leg; a sign of nail piercing on his left leg; sign of flogging on his back
  4. Tofik Shikur – a scar on his right hand; uprooting of both thumbs of his legs’ nails; a scar on his left hand
  5. Shemsu Seid – signs that look like remains of flogging at his back
  6. Misbah Kedir – Scar-marks left from handcuffs; a large scar on his right hand; a small scar on his left hand; scars on both of his right and left legs thighs; breaking of his right hand’s pointing finger
  7. Fitsum Getachew – Right hand injury
  8. Temesgen Markos – breaking of his right hand and a scar; large scars on both of his legs
  9. Ashenafi Melese – scars on both of his right and left legs; breaking of his right hand’s ring-finger
  10. Kassa Mohammed – deep scar on his right hand; injury on his head
  11. Sisay Batu – a scar on his right hand
  12. Abduldafar Asrat – uprooting of both of his legs’ thumbs’ nails
  13. Dereje Merga – six scars on his left leg; scar-marks left from handcuffs on both of his legs
  14. Tofik Ferha – a scar on his left hand; scar-marks left from handcuffs
  15. Omar Hassan – uprooting of right leg thumb’s nail; uprooting of nail of next to thumb in his left leg
  16. Seifu Girma – a scar after nail piercing on his left back shoulder; scars on both of his legs

Victims’ Responses

In a five pages of letter smuggled out of prison, the defendants have drafted their opinions on their case, complaints on their current treatment by prison admins and also their response to EHRC’s investigative report. Their response to EHRC’s report is mixed with feelings: they are partly glad EHRC didn’t deny it all as it is a culture in state institutions (at least in perceptions of citizens), on one hand; and, they think it revealed only a small part of what was done against them, on the other hand. Here is what they said:

  1. EHRC didn’t include all human rights violations perpetrated against us
  2. EHRC didn’t request for the accountability of perpetrators of the violations apart from forwarding ‘proposals’ of further investigations in obvious fear of the executive powers
  3. EHRC’s proposal for Addis Ababa Police Commission and Medical Center to further investigate the violations is like giving the violators of our rights an exit from being held accountable
  4. Regardless of all these, we are GRATEFUL to EHRC because it gave us a document that proves our confession to police according to Criminal Code Procedure 27/2 was forced and that it was not genuine confession
Screenshot of from the letters by the victims.

The victims also made calls to all media, human rights organizations, activists, diplomats and every citizen who is concerned about justice to follow their case. 

We less often discuss personalities that are fertile grounds either to be ruled by authoritarians or to be one of them. But, I think, it is important to look what is in them as it looks like we dont basically change from the way our parents have raised us. Our ancestors were either members of the oppressors or the majority (the oppressed) in the past, so are we. It happens to be we use that same privilege inherited from our parents to advance others; or, to remain underprivileged. History proves it is most probable that off springs follow their ancestors footsteps. Chances are big that children of the poor will remain poor; children of farmers remain farmer; children of democratic societies will remain democrat and etc. And, all this is until the quagmire breaks at some point. What’s keeping us a conformist? And, how can we break it?
I was reading a book titled “Between the World and Me” authored by Ta-Nehisi Coates and found some childhood experiences were shared between his world and mine. He wrote his father used to beat him out of fear, “My father was so very afraid. I felt it in the sting of his black leather belt, my father who beat me as if someone might steal me away, because that’s exactly what was happening all around us. Everyone had lost a child, somehow, to the streets, to jail, to drugs, to guns.” Thousands of miles away to Coates’ place, my mother had felt similar fear. My mother used to mention youngsters from my neighborhood and say I should not be like  them. By beating me, she thought she was protecting me. 
Until the age of 11, our father used to live far from us. Therefore, all the burden of raising us (the children) was laid on our mother’s shoulders. And, she was always worried that we may be called woman’s children”, negatively perceived saying to mean ‘undisciplined’. As a child, all I remember was that she always beat me for every little mistakes I made and sometimes to the possible mistakes I could have done. Our mother still believe she has done right and makes pride out of it claiming that we (her children) are well disciplined because she shaped us in terms of physical punishment. 
I was also beaten in Maekelawi, Ethiopia’s torture chamber for the past three regimes. I have always asked what the people who do tortures (as a job) there feel about it. I’m sure they tell themselves an excuse to do that. They may be feeling they have to do it for the wellbeing of the country, or of the people. Basically, the excuses do not have essential difference as to why our parents and teachers beat us while we were children. They want to protect us from ourselves, from our environment and from the world we live in. 
The discovery of ‘Authoritarian Personality’
Based on nature-nurture influence, psychologists define personalities in many categories. But, the so-called ‘Authoritarian Personality’ is discovered following the holocaust in the Second World War. Psychologists asked how a lot of people could accept it, and a group of American based social scientists, led by Theodor Adorno, came up with a researched answer in a book titled  ‘Authoritarian Personality’ (published in 1950). According to their findings, people with an ‘Authoritarian Personality’ tended to be:
  • Hostile to those who are of inferior status, but obedient of people with high status;
  • Fairly rigid in their opinions and beliefs;
  • Conventional, upholding traditional values.
In Ethiopia, especially in urban life, it used to be a common practice to beat children in an excuse of raising them well disciplined. It is still not stopped totally. Children are beaten by their parents, by their teachers and almost by everyone who is an elderly. 
Psychologist Theodor Adorno and his team found in a study that “people with ‘Authoritarian Personalities’ were more likely to categorize people into us and them groups, seeing their own group as superior”; and also that “individuals with a very strict upbringing by critical and harsh parents were most likely to develop an authoritarian personality.” This maybe a reason why most people in Ethiopia appear ethnocentrist and justify authoritarianism. 
People with ‘Authoritarian Personality’ are said to show these characteristics:
  • Ethnocentrism, i.e. the tendency to favor one’s own ethnic group;
  • Obsession with rank and status;
  • Respect for and submissiveness to authority figures;
  • Preoccupation with power and toughness.
Saying No to the Way We Were Made
Fortunately, individuals can beat social norms and learn to see out of box. Trends get broken. People change. 
In addition, ‘Authoritarian Personalities’ are not absolute. In critical evaluation of Adorno’s analysis of ‘Authoritarian Personality’, there are many points psychologists raise in response to his explanation of prejudice:
  • Harsh parenting style does not always produce prejudice children/individuals;
  • Some prejudice people do not conform to the ‘Authoritarian Personality’ type; and
  • Doesnt explain why people are prejudiced against certain groups and not others.
Similar experiences affect different people differently. Ta-Nehisi was not stolen by either of the streets, drugs or guns like his father was afraid. The same happened to me. But, I don’t say the beating worked. Because, when I grow up I have, one by one, dropped the norms my parents valued most. Religion is one of the most valued norms in our family. To declare that I don’t anymore believe in Christianity nor existence of a creator is something my mother would never want to hear. But, it happened. So many things happened different to my parents expectation. I do believe I stopped categorizing myself into ‘us’ and ‘them’. I hope and guess my deviation is also in terms of respect to liberty of myself and of others. I hope I have also deviated from the ‘Authoritarian Personality’ that I was raised into because, eventually, the choice is mine. It is by beating fear, not our children nor people whom we thought are dangerous, that we can win authoritarianism, consequence of fear itself.  

ከዓመታት በፊት አንድነት ፓርቲ በሕይወት ሳለ፣ የቀድሞዎቹ የኢሕአዴግ ባለሥልጣናት አቶ ስዬ ኣብርሓ እና ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ፓርቲውን ሊቀላቀሉ ሲሉ ትልቅ ፌሽታ ሆኖ ነበር። እንዲያውም ‘መርሕ ይከበር’ በሚል የተገነጠለው ቡድን፣ እነርሱን ለመቀበል የተዘጋጀውን ድግስ በአመፅ እስከማደናቀፍ ደርሷል(?)። ቅራኔው “እነርሱ የተለየ አቀባበል የሚደረግላቸው የገዢው ፓርቲ የቀድሞ አባል ስለሆኑ ነወይ?” የሚል ነበር። ተቃዋሚው የቀድሞ የኢሕአዴግ አባል ለቅቆ ሲወጣ ማግነን ያውቅበታል። በአንድ በኩል ሳስበው፣ መቃወማቸው ትክክል መሆኑን የገዢው አባላት መልቀቅ ለተቃዋሚዎቹ ስለሚያረጋግጥላቸው ይመስለኛል። በሌላ በኩል ደግሞ፣ ከጥቅም ባሕር ውስጥ መውጣት ስለሚከብድ ያንን እያሰቡ ይመስለኛል። የኋለኛውን እንዳላምን እንደ ዶ/ር ነጋሶ፣ ከጥቂቶቹ በቀር ብዙዎቹ ተገፍተው ነው ከገዢው የሚወጡት።

የሆነ ሆኖ፣ አናንያ ሶሪ በስላቅ እንደተናገረው፣ ‘ብለን ብለን ኦሕዴድ እና ብአዴን ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ ዛሚ እና ENN ነጻ ሚድያዎች የሆኑበት ዘመን ላይ ደርሰናል’። ለማንኛውም በምናገባኝ ነገሩን ከመታዘብ ይልቅ የኦሕዴድ (እንዲሁም የብአዴን) የሰሞኑ እምቢተኝነት እውነት ወይስ የሕወሓት ሴራ? ተቃዋሚው (በፓርቲ የታቀፈውም ያልታቀፈውም) ጉዳዩን እንዴት ነው ማስተናገድ ያለበት? የሚሉትን ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት እንሞክር።

የጠላቴ ጠላት ለኔ ምኔ?

በተቃዋሚዎች ዘንድ “የሕወሓት የበላይነት” መኖሩ እምብዛም አጠራጣሪ አይደለም። ማኅበራዊ ሚድያ አሁን (ከተዳራሽነቱ በላይ) በኢትዮጵያ ፖለቲካ የሐሳብ አቅጣጫ አስማሪ እንደመሆኑ ይህንን እምነት የበለጠ በማስረፅም ሆነ በመታገል ረገድ የጉዞ ካርታ (road map) አስቀማጭ ነው። ይህንን ብዙዎች መረዳታቸው ሽሚያ ፈጥሯል። መጀመሪያ ታሪክን፣ ከዚያ ድልን፣ አሁን ደግሞ ሟችና ገዳይን መሻማት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በዚህ መሐል የሕወሓት ደጋፊ/ካድሬዎችም የራሳቸውን ትርክት ይፈጥራሉ። ተቃዋሚው ደግሞ እነርሱ የወደዱትን መጥላት፣ እነርሱ የጠሉትን መውደድን እንደ ምላሽ ይገብራል። አንዳንዴ ሳስበው የሕወሓት ካድሬዎች ተቃዋሚው የሚፈልጉትን እንዲያደርግላቸው ከፈለጉ፣ ያንን ነገር እንዳያደርገው መቀስቀስ ብቻ የሚበቃቸው ይመስለኛል። “ገዱን የምወደው ሕወሓት ስለምትጠላው ነው” የሚል መፈክር ሰምቻለሁ። አቶ ገዱ በሕወሓት ካድሬዎች ፌስቡክ ላይ ከመተቸታቸው በቀር ፓርቲያቸው (ብአዴን) በሕወሓት እልቅና የሚተዳደረው ኢሕአዴግ አባል ነው። የኦሕዴድ የሰሞኑ ነገርም ያው ነው። ይህ ዓይነቱ ምክንያት ለብአዴንም ይሁን ለኦሕዴድ የድጋፍ መሠረት ሊሆኑ አይችሉም።

ኦሕዴድ እና ብአዴን እውን ሕወሓት ላይ አምፀዋል?

ከአስቸኳይ ግዜ አዋጁ በፊት ፌዴራል ፖሊስ የኦሮምያ ከተሞችን መናኻሪያው ሲያደርገው፣ በአማራ ከተሞች ግን (ቢያንስ ተቃውሞዎችን ለመበተን) አልገባም ነበር። የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ በታወጀበት ወቅት የሚበዙት እስረኞች የታፈሱት ከኦሮሚያ አካባቢ ነበር። ሌላው ደግሞ እነ ኮሎኔል ደመቀን ለፌዴራል መንግሥቱ አሳልፎ ባለመስጠቱ፣ በዚያ ላይ ብአዴን በላዕላይ ደረጃ ሹም ሽረት ባለማድረጉ፣ በተወሰነ ደረጃ ብአዴን የክልሉን ነጻነት (autonomy) እያስከበረ ነው ማለት ነው በሚል ወስጄው ነበር። ይሁን እንጂ የኋላ ኋላ በአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ወቅት የክልሉን ነዋሪዎች ትጥቅ የማስፈታቱ ሥራ በፌዴራሉ የፀጥታ ኃይሎች በዝምታ እንደተሠራ ሰማሁ። እንዲሁም ከክልሉ ታፍሰው መቐለ፣ ባዶ ሽድሽት ታስረው የተፈቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አባሎች አግኝቼ የክልሉ ነጻነት (ወይም የአቶ ገዱ እና ፓርቲያቸው እምቢተኝነት) ላይ ያለኝ የማመን ዝንባሌ ቀስ በቀስ ተገፈፈ። በርግጥም አሁን፣ የሕወሓት ካድሬዎች ስሞታቸውን ከብአዴን ላይ አንስተው ወደ ኦሕዴድ አዙረዋል። ኦሕዴድም በተራው ደጋፊ እየጎረፈለት ነው።

ኦሕዴድ በተቃዋሚዎች ዘንድ ሳይቀር ተአማኒነት እንዲያገኝ ያደረገው በኦሮሚያ ሶማሊ ክልሎች ድንበር ነዋሪዎች ዘንድ በተደረገው ግጭት ላይ፣ የክልሉ መንግሥት ባሳየው ለክልሉ ነዋሪዎች ያደላ ተቆርቋሪነት ነው። በዚህ ላይ የሶማሊ ክልል መንግሥት ያንፀባረቀው ብስለት የጎደለው ምላሽ ግጭቱን በማባባስ፣ የኦሕዴድን ተቀባይነት ጨምሮታል። የሶማሊ ክልል ገዢ ፓርቲ (መንግሥት) የ2008ቱን ሕዝባዊ አመፅ ከመቃወም ጀምሮ፣ ያሳየው ዝንባሌ በሕወሓት ወዳጅነት አስፈርጆታል።
ስለዚህ ከሶማሊ መንግሥት ጋር የኦሮሚያ መንግሥት መጋጨቱ፣ ኦሕዴድ ሕወሓትን እንደደፈረ ተደርጎ ተተርጉሟል። በተለይ እኔ ራሴ ቢሾፍቱ ተገኝቼ ባየሁት የኢሬቻ በዓል ላይ እና ከዚያ በኋላ በተካሔዱ ተቃውሞዎች ላይ የክልሉ ፖሊስ አንድም እርምጃ አለመውሰዱ፣ ቀድሞም እነጃዋር “ገዳያችን አግኣዚ ነው” የሚሉትን ተአማኒ አድርጎታል። ለኦሕዴድም ግርማ አላብሶታል።

የኢሕአዴግ አባሎች እንቢታ ምን ፋይዳ አለው?

“የሕወሓት የበላይነት” በፌዴራል መንግሥቱ ብቻ ሳይሆን በኢሕአዴግ ውስጥም አለ። ይህ የሚጀምረው ከአመሠራረታቸው ነው። የኢሕአዴግ አባል ፓርቲዎች፣ በሕወሓት ፍላጎትና ርዕዮተዓለም ተጠርበው፣ ለሕወሓት በኦሮሚያ፣ አማራ እና ደቡብ ክልሎች ቅቡልነት ለማስገኘት የተፈጠሩ ቡድኖች ናቸው። ‘እነዚህ የግንባሩ አባላት የሚያደርጉት ‘መፈንቅለ ሕወሓት’ ተረኛ ጨቋኝ ከማምጣት ውጪ ምን ያመጣሉ?’ የሚል ጥያቄ መነሳቱ አይቀርም።

አምባገነን ገዢን ለመጣል የሚደረገው ትግል ብዙ ፈርጅ አለው። አንዱ አማራጭ ቡድን አቅርቦ ሕዝቡ እንዲመርጠው ማድረግ ነው። ሌላው፣ ገዢው ፓርቲን ሕዝቡ እንዳይቀበለው ማድረግ  ነው። ኢሕአዴግ አማራጭ ኃይሎችን በሚችለው መንገድ ሁሉ ያዳክማል። ተቃዋሚዎች ግን የማዳከም ዕድሉን ለማግኘት እንኳን ሲሞክሩ አይታዩም። በ2008ቱ የኦሮሞ ሕዝብ አመፅ ወቅት ግን የኦሮሞ አክቲቪስቶች ለደረሰው ጥፋት ሁሉ የክልሉን መንግሥት በመውቀስ ፈንታ አግኣዚ እና ሕወሓትን ላይ በማሳበብ በስተመጨረሻ፣ በከፊልም ቢሆን የታችኛው የኦሕዴድ ካድሬዎችን ልብ ከሕወሓት መነጠል ችለዋል። ኦሕዴድን ከሕወሓት መነጠል፣ ወይም ውስጣዊ ነጻነቱን እንዲያስከብር መቻል ለተቃዋሚው የራሱን ዕድል ይሰጣል። ስለዚህ ተቃዋሚው ከዶግማዊ ተቃውሞ ወይም ድጋፍ ይልቅ፣ ስልታዊ ድጋፍ እና ተቃውሞ ማድረግ ለድል ያበቃዋል የሚል እምነት አለኝ። ጥያቄው መሆን ያለበት፣ ‘ድጋፉ ከስልት አልፎ ሙሉ እምነት ዕድሜ ልካቸውን ሲጨቁኑ ወይም ለጨቋኝ አሳልፈው ሲሰጡ የነበሩት ላይ መጣል ደረጃ ተደርሷል ወይ?’ የሚለው መሆን አለበት።

በፌስቡክና ትዊተር ላይ ለኦሕዴድ የቀረበለትን ድጋፍ እየተመለከትኩ ነበር። ለድጋፍ የሚቀርቡትን ምክንያቶች እንደሚከተለው አዋቅሬያቸዋለሁ፦

፩ኛ፣ ኦሕዴድ በአሁን ይዞታው የኦሮሞን ጥቅም ለማስጠበቅ ብቁ ነው በሚል፤
፪ኛ፣ የግንባሩ ውስጥ-ለውስጥ ትግል ኢሕአዴግን ያፈርሰዋል/ያዳክመዋል (በዚህም ተቃዋሚው የመጠናከር ዕድል ያገኛል) በሚል፤
፫ኛ፣ በፓርቲ ውስጥ ያለው የሕወሓት የበላይነት መቀረፍ፣ በፌዴራል መንግሥቱ ውስጥ ያለውን የበላይነትም ይቀርፈዋል በሚል፤
፬ኛ፣ ታሪካዊ ብሶት የሌለበት አናሳ ቡድን ከሚጨቁነኝ፣ ታሪካዊ ብሶት ያለበት ብዙኃን ቡድን ቢጨቁነኝ ይሻላል በሚል፤
፭ኛ፣ ኦሕዴድ “የኛው” (የኦሮሞዎች) ስለሆነ ከቀናው ተረኛ መሪ እንዲሆን ዕድሉን እንስጠው በሚል፤
፮ኛ፣ ሌሎች…

በተመሳሳይ፣ የኦሕዴድን ማፈንገጥ (ያፈነገጠ መምሰል) ያልተቀበሉት፦

፩ኛ፣ የኦሕዴድ (የብአዴንም ሊሆን ይችላል) ‘ያፈነገጠ መምሰል’ የሕወሓት የፖለቲካ ሴራ ነው ብለው ያመኑ፤
፪ኛ፣ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች በተፈጥሯቸው ሊለወጡ የማይችሉ ናቸው የሚሉ፣
፫ኛ፣ የግንባሩ አባላት የፈለገ ቢለወጡ ምንም ዓይነት ይቅርታ ሊደረግላቸው አይገባም የሚሉ፣
፬ኛ፣ ሕወሓት በመከላከያ እና ደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ያለው ቁጥጥር የእነኦሕዴድን መፍጨርጨር የትም አያደርሰውም እና ጉልበት እነርሱ ላይ ማባከን አያስፈልግም የሚሉ፤ እና፣
፭ኛ፣ የተለያየ ምክንያቶች የሚሰጡ ናቸው።

አፈንጋጭ የተባሉትን ምንም ዕድል ለመስጠት ፈቃደኛ የማይሆኑት በፖለቲካ ዓለም ቋሚ ወዳጅ ወይም ቋሚ ጠላት የሚባል እንደሌለ የዘነጉ ይመስላሉ። ግዚያዊ ወዳጅነቶች/ጠላትነቶች ለሚያራምዱት ርዕዮተ ዓለም ካለው ፋይዳ አንፃር ነው መገምገም የሚኖርባቸው። ሁሉን ነገር የሕወሓት ሴራ ነው ብሎ ማሰብ ሕወሓት የገዘፈ ብልሐተኛ የማድረግ አባዜ ይመስለኛል። ኢሕአዴግ ብልሕ እየሆነ ከሆነም ከሱ በላይ ብልሕ ሆኖ መገኘት ያስፈልጋል። ይህ ሕወሓትን የተወሳሰበ የፖለቲካ ጫወታ ባለቤት ማድረግም ይሁን የገዢው ፓርቲ አባላትን ሲለቅቁ እልል ብሎ መቀበል፣ ከራስ ይልቅ ለኢሕአዴግ ያለን የተደበቀ እምነት አሳባቂ ይመስላል።

ሕወሓት ለምን ዝም አለ?

ብአዴን ሲተብት፣ ኦሕዴድ ሲያፈነግጥ – አለቃ ተብዬው ሕወሓት ለምን ዝም አለ? እስኪ ማን ማን እንደሚያፈነግጥ ልያቸው እና ለቃቅሜ ልክ አስገባቸዋለሁ ብሎ ነው? ወይስ፣ የራሱ ሴራ ስለሆነ (በዚህ አጋጣሚ ተቃውሞው ስለታገሰለት፤ እንዲሁም ዳያስፖራው ከጫወታ ውጪ ስለሆነ) ደስ ብሎት ነው? እነዚህን ጥያቄዎች በአሻጥር ትንተና ሳይሆን በተጨባጭ ማስረጃዎች መገምግም ያስፈልጋል። በመልሱ ላይ ተመሥርቶ ስልታዊ ድጋፍ/ተቃውሞ ማድረግ ይከተላል። የአሁኑ ግን ጭፍንነት ይበዛዋል ባይ ነኝ።

የኦሕዴድ ኅብረ ዝማሬ ምንጩ ምንድን ነው?

የኦሮሞ ፖለቲከኞች ‘በአንድነት ኃይሎች’ በጠባብነት እና በተገንጣይነት የመፈረጃቸው ነገር ያደባባይ ምሥጢር ነው። ነገር ግን የምር ኢሕአዴግ ውስጥ ሕወሓትን ለመቀናቀን ከፈለጉ አንድ አጋር ያስፈልጋቸዋል። ፈዛዛው ደኢሕዴን የሕወሓት ካርድነቱ አሁንም እንደቀጠለ ነው። ስለዚህ ከብአዴን ጋር መተባበሩ የግድ ነው። ኦሕዴዶች ጉባኤያቸው ላይ ባሳለፉት አቋም፣ በሚሰጧቸው መግለጫዎች ለኢትዮጵያዊ ኅብረት ያላቸው ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ መግባት እንደሌለበት በመሐላ እያረጋገጡ ነው። 7ኛ መደበኛ ጉባዔያቸው ላይ አቋም ከወሰዱባቸው ነጥቦች አንዱ “የኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም እና የኢትዮጵያውያንን ኅብረት ጉዳይ የማይደራደሩበት” መሆኑን ገልጸዋል። የጥቅምት 25-27ቱ የምክክር መድረክ ዓላማም ይኸው ይመስለኛል። (ከታች ሶልያና ሽመልስ በትዊተር ላይ የኦሕዴድ-ብአዴንን የሰሞኑን ኅብረት የሚደግፉት ሰዎች ለምን እንደሚደግፉት የጠየቀችበትን ፖል ውጤት አስቀምጣለሁ፤ ብዙዎቹ “ለኢትዮጵያ አንድነት ይጠቅማል” በሚል ተስፋ ነው ድጋፋቸውን የሰጡት።)

ብዙዎቹ መልስ ሰጪዎች የሁለቱን ድርጅቶች
ኅብረት የሚደግፉት ኢትዮጵያዊ አንድነትን ተስፋ
አድርገው ነው። የኦሮምኛ እና እንግሊዝኛው
ፖልም ተመሳሳይ ውጤት ነው ያላቸው።

ከመደምደሜ በፊት ግን የኦሕዴድ-ብአዴን ጥምረትን ለሚደግፉ ሁለት ማስጠንቀቂያዎችን አኖራለሁ፦ አንደኛ፣ የሁለቱ ቡድኖች ጥምረት ከሠመረ ዴሞክራሲ ሊያመጣ የሚችል የመሆኑን ያክል፣ የብዙኃን ገነንነት (majority dictatorship) ሊያመጣ የሚችል እንደሆነ እንዲያስቡበት፤ ሁለተኛ፣ ተቃዋሚዎች ድጋፍ ወይም ተቃውሟቸው ሙሉ ለሙሉ በሁለቱ ፓርቲዎች ላይ ጥገኛ አድርጎ እንዳያስቀራቸው እና መርሕ-መር መሆን እንደሚኖርበት ሁሌ ራሳቸውን ማስታወስ እንዳይዘነጉ ነው።

ከሁሉም በላይ ግን ይህ በሕዝብ አመፅ የተገኘ ዕድል ለኦሕዴድ እና ብአዴን የሥልጣን መወጣጫ እርካብ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር መትጋት ያስፈልጋል።

አግባብ ያልሆኑ እስሮች፣ ያልተጠበቁ ፍቺዎች እና የማይታመኑ የፍቺ ክልከላዎች ደጋግመው ቢከሰቱም ሁሌ እንደ አዲስ የሚያወያዩን አጀንዳዎች ናቸው። ኦቦ በቀለ ገርባ የታሰሩት የኦሮሞ ሕዝብን ጥያቄ ያለ ፍርሐት ስላስተጋቡ ብቻ ነው። ይህን የምለው ለይስሙላ አይደለም፤ የፌዴራል ዐቃቤ ሕግ ያቀረበባቸውን ማስረጃ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ አራተኛ ወንጀል ችሎት ተገኝቼ አድምጬያለሁ። ችሎቱ ክሳቸውን ከሽብር ወደ ‘በንግግር አመፅ ማነሳሳት’ (የወንጀል ሕጉ አንቀፅ 257/ሀ) ዝቅ ሲያደርገው ዋስትና እንደሚያሰጣቸው ግልጽ ነበር። ችሎቱ በዋስትና ጉዳይ ውሳኔ ለመስጠት ከአንድ ቀጠሮ በላይ ሲወስድ አይቼ አላውቅም። እርሳቸውን ግን ደጋግሞ ቀጠሮ ሲሰጣቸው፣ ዳኞች ዋስትናውን መከልከልም ሆነ መፍቀድ የፈሩ ይመስል ነበር። በመጨረሻ የሞት ሞታቸውን ከለከሏቸው እና አረፉ። ይግባኝ ተባለ፣ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ30 ሺሕ ብር የስር ፍርድ ቤት የከለከለውን ፈቀደ። ቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ ቤት እስረኛውን በመፍታት ፈንታ ደብዳቤው ላይ የተጻፈው ቁጥር አደናገረኝ በሚል ሰበብ ሁለት ቀን አሳደራቸው። በመሐል ፋና ሬዲዮ የኦቦ በቀለ ፍቺ በዐቃቤ ሕግ ይግባኝ ባይነት፣ በሰበር ሰሚ ችሎት ታገደ የሚል ዜና ይዞ ወጣ። Déjà vu. 
ሐምሌ ወር 2007፣ በእነዘላለም ወርቅአገኘሁ መዝገብ ሀብታሙ አያሌው፣ አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ዳንኤል ሺበሺ እና አብርሃም ሰለሞን ነጻ ከተባሉ በኋላ የተከሰተው ይሄንኑ ይመስል ነበር። ቤተሰቦቻቸው ሲፈቱ ለመቀበል ቂሊንጦ በር ላይ ሲመላለሱ፣ ማረሚያ ቤቱ ሰበብ ሲፈጥር አቆያቸው፤ በመሐል፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፍቺያቸውን እንዳገደው ተሰማ። ከዚያ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ በዞን ዘጠኝ ጉዳይ ከታሰሩት አምስቱ ድንገት ስማቸው ተጠርቶ ከቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ ቤት ተጠርተው ውጡ ተብለው ነበር። ለቀሪዎቹም ሆነ ለወጪዎቹ በጣም አስደንጋጭ ገጠመኝ ነበር። ዐቃቤ ሕግ የነዚህን አምስቱን ክስ አንስቷል ተባለ። ከሁለት ሳምንት በኋላ ቀሪዎቻችን ፍርድ ቤት ቀረብን፣ ያኔ “ተከላከሉ ወይም በነጻ ተሰናበቱ” መባል ነበረብን። ቀጠሮ ተሰጠን፣ ተደገምን፣ 5 ጊዜ። ጥቅምት የሞት ሞታቸውን ቀሪዎቻችን ፈቱን። የነ ሀብታሙ ጉዳይ በጠበቃቸው ይግባኝ ባይነት ዓመት ያክል ተንዘላዝሎ፣ እነርሱም ተፈቱ። 
ማነው አሳሪ?
ለዚህ ጥያቄ እርግጠኛ መልስ ማግኘት ይከብዳል። ከልምድ ግን መገመት ይቻላል። እኔና ጓደኞቼ ማዕከላዊ በነበርንበት ጊዜ ማዕከላዊ የነበሩት (በቁጥጥር ሥር ያዋሉን) መርማሪ ፖሊሶች ስለኛ የሚያውቁት ጥቂት ነገር ነበር። ወረቀታቸውን እያገላበጡ ሲጠይቁን፣ የሆነ ከጀርባቸው ያለ ሰው እነዚህን ጥያቄዎች ጠይቋቸው ብሎ እንደላካቸው ያስታውቅባቸው ነበር። በሰጠናቸው መልሶች የረኩ መስለው ከሔዱ በኋላ፣ እሳት ለብሰው እሳት ጎርሰው ይመለሳሉ። መልሳችን የላኳቸውን ሰዎች አላረካም ማለት ነው። ይሔ ነገር ለኔ ያመላከተኝ ቢኖር ከኋላቸው አለቆቻቸው መኖራቸውን ሳይሆን፣ የአለቆቻቸውም አለቆች መኖራቸውን ነው። በኔ ግምት ‘የመረጃ እና ደኅንነት ቢሮ’ (ደኅንነቶች) ከሁሉም የሽብር ነክ እስሮች ጀርባ ናቸው። 
ጠበቆች አዲስ ክሶች በተመሠረቱ ቁጥር ‘የሕግ ባለሙያ እንዴት እንዲህ ዓይነት ክስ ያዘጋጃል?’ እያሉ ይገረማሉ። ዐቃቤ ሕጎች፣ ለችሎት ‘ክሱን አላየሁትም አሁን ነው የደረሰኝ’ ሲሉ ሰምቼ አውቃለሁ። የሚሰጡት ሰበብ ‘ዐቃቤ ሕግ ተቋም ነው፤ አንዱ ያዘጋጀውን ክስ ሌላው ያስቀጥለዋል’ የሚል ቢሆንም አያሳምነኝም። የሽብር ክሶቹን የሚጽፋቸው ረዥም እጅ ያለ ይመስለኛል – ይኸውም ሊሆን የሚችለው የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ብቻ ነው። 
የዳኞች መለማመድ
የሽብር ችሎትን መዳኘት ሕሊና ላለው የሚያሰቃይ ነገር ነው። አብዛኞቹ ተከሳሾች የአሰቃቂ ጥቃት ሰለባ ናቸው። ያንንም ሰሚ ባገኝ በሚል ተስፋ በችሎት ይተነፍሱታል። ክሱ ዝርክርክ ነው። ማስረጃዎቹ አይረቡም። ተከሳሾቹ በችሎቱ ነጻነት አያምኑም። ዳኞቹ በተለያዩ ጊዜዎች የተለያዩ ስሜቶችን ሲያስተናግዱ ይቆዩና ወደኋላ ላይ የተከሳሾቹን ሕመም መረዳት፣ ማባበል፣ ለውሳኔያቸው ረዥም ማብራሪያ መስጠት እና ፈራ ተባ እያሉ አንዳንድ እስረኞችን መፍታት ይጀምራሉ። ወዲያው ግን ይቀየራሉ።  የሽብር ችሎቶች ዳኞች በጣም ቶሎ፣ ቶሎ ከመቀያየራቸው የተነሳ አንዱ የጀመረውን ጉዳይ ሌላ የመጨረሱ ዕድል ሰፊ ነው። 
በገዢዎቻችን እና በዳኞች መካከል ያለውን ግንኙነት ከውጭ ምልከታ ለመመዘን ሞክሬያለሁ። በቀጥታ ‘እከሌን ይሄን ያክል ፍረድበት፣ እከሌን ፍታው’ የሚባሉ አይመስለኝም። ነገር ግን ዳኞቹ ሲሾሙ መጀመሪያ ለስርዓቱ ያላቸው ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ መግባት የለበትም። አንዳንዶቹ ለገዢው ቡድን ጥብቅና ይሰማቸዋል። በዚያ ላይ ሹመቶች አሉ። በታማኝነታቸው ልክ ነው ቀደምቶቹ የተሾሙት።  በሌላ በኩል፣ በተለይ በሽብር ጉዳይ፣ ተከሳሾች የሚመሠረትባቸው የክስ አንቀፅ በራሱ መልዕክት ነው። አሳሪው ተከሳሹን ምን ያህል ማሰር እንደሚፈልግ በክሱ ያመለክታል። በዚያ ላይ የግል ፍርሐታቸው አለ፤ ‘መንግሥት በዚህ የጠረጠረውን እኔ እንዴት ማስረጃ የለም ብዬ እፈታዋለሁ?’ ከዚያም ውጪ ምናልባት በውስጥ ስብሰባቸው ላይ ‘ጉዳዩ ሲሪዬስ ነው’ ይባሉ ይሆናል። ለዚህም ይመስለኛል፣ ዳኞች ከእስረኞቹ ጋር ሲለማመዱ፣ ሐዘኔታ ሲሰማቸው፣ መተዋወቅ ጥርጣሬያቸውን እያጠፋ የመፍታት ድፍረታቸው ሲጨምር አስተዳደሩ የሚፐውዛቸው። አሁን ለምሳሌ የአራተኛው ወንጀል ችሎት ሦስቱም ዳኞቹ ከዚህ ወር ጀምሮ ተቀይረዋል። የ19ኛው ችሎት ዳኞችም በቅርቡ ተቀያይረዋል።
ከዚያ ውጪ ያለው ጫወታ በዐቃቤ ሕግ ሥም ነው። ሲያሻቸው ክሱን ያከብዱታል፤ ሲያሻቸው ያቀሉታል። ሲያሻቸው ክሱን ያቋርጡታል። ሲያሻቸው ምስክሮችን በማፈላለግ ሥም የችሎቱን መደመጥ (እስኞቹ ወኅኒ ተጥለው) ያራዝሙታል (ለዚህ ተባባሪያቸው ምስክሮቹን ማቅረብ ያለበት ፖሊስ ነው)። ሲያሻቸው ፍቺውን በይግባኝ ያሳግዱታል (ለዚህ ደግሞ ተባባሪዎቻቸው የማረሚያ ቤት አስተዳደሮች ናቸው)። 
ማረሚያ ቤቶች ውስጥ የፍቺ ወረቀት መጥቶለት እንዲቆይ የሚፈልጉት ሰው ላይ ሰበብ ይፈጥራሉ። ማረሚያ ቤቶች ውስጥ “ደኅንነት” የሚባሉ ሠራተኞች አሉ። የሥራ ድርሻቸው ምን እንደሆነ አይታወቅም፤ ግን ፈላጭ ቆራጭ ናቸው። እንደሚመስለኝ፣ ዐቃቤ ሕጎች ይግባኝ እንዲሉ (ደኅንነት መሥሪያ ቤቱ) ሲወስን፣ በቀጥታ ለማረሚያ ቤቶቹ የደኅንነት ሠራተኞች፣ እስረኞቹ በሰበብ እንዲቆዩ ትዕዛዝ ይሰጧቸዋል። በዚህ ግዜ ከላይ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ይፈፀማል። ዐቃቤ ሕጎች ይህንን በራሳቸው አይፈፅሙትም ብዬ የምገምተው በምክንያት ነው። አብዛኛዎቹ ወጣቶች ናቸው። ካልታዘዙ በቀር በሥራው ላይ እስከ ይግባኝ ለመሔድ የተዘጋጀ ምንም የሥራ መነቃቃት አይታይባቸውም። እንዲሁ ሥራ አጥተው የገቡ ስልቹዎች ናቸው። ብዙውን ክስ አያውቁትም፤ እንዲያውም ችሎት ውስጥ ሲነበብ ከታዳሚው ጋር እየሰሙ የትየባ ስህተት ገጥሞ እንዲያርሙት ሲጠየቁ ግራ ይጋባሉ።
ታዲያ ማነው ፈቺ?
ድንገት ክሳቸው ተቋርጦ የተፈቱ ሰዎች፤ የሞት ፍርድ፣ የ22 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው በ6 ወይም በ3 ዓመታቸው የተፈቱ ሰዎች አሉ። ይቅርታ ጠይቀው ያልተፈቱ አሉ፤ ይቅርታ ጠይቀው የተፈቱ አሉ። ይቅርታ ሳይጠይቁ የተፈቱ አሉ። መታሰራቸውም አግባብ ስላልነበር፣ መፈታታቸው ብዙዎቻችንን ያስደስተናል። ግን ማነው የሚፈታቸው? በምን መመዘኛ?  የማረሚያ ቤቱ ሥልጣን፣ ከፍርድ ቤቱ ይለያል። ነገር ግን ፍርድ ቤት “የእስረኞችን መብት አትጣስ” ሲባል ጆሮ ዳባ ልበስ የሚለው እና ባለፈው ዓመት የአራተኛው ወንጀል ችሎት ዳኞች “እኛን አትሰሙንም” ብለው ያማረሩት ማረሚያ ቤት ሥልጣን አለው እንዳይባል፤ የለውም። በቀድሞ ታጋዮች የሚመራው ማረሚያ ቤት ለሽብር እስረኞች ከፍተኛ ጥላቻ አለው። ሥልጣን ቢኖረው ስንቶቹ የሙስና እስረኞች (ከቀድሞ ታጋዮችም አሉበት) ለአስተዳደሮቹ በሚሰጡት መደለያ ብዛት ቀዳሚው ተፈቺ ይሆኑ ነበር። ስለዚህ ፈቺ አሁንም የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ነው። መፈታትም የነጻነት፣ ወይም የእስር ዘመንን ማረጋገጫ ሳይሆን የፖለቲካ ጫወታ ነው። አንዳንዴ እየከፋፈሉ እያሰሩ፣ እየከፋፈሉ መፍታት። ሌላ ግዜ ስጋት የሆነውን አቆይቶ፣ ስጋት ያልሆነውን  በመፍታት መደለል። ሌላም፣ ሌላም…
ከዚህ ውጪ ያለው ግምት ብዙም አይስማማኝም። ምክንያቱም፣ አሳሪም የደኅንነቱ ቢሮ፣ ፈቺውም የደኅንነት ቢሮ።

ብዙ ሰው ችላ ብሎታል። የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ግን “መደራደራቸውን” ቀጥለዋል። ከኢሕአዴግ ጋር እየተደራደሩ ያሉት ፓርቲዎች ምንም ሕዝባዊ ቅቡልነት/ውክልና የላቸውም ማለት ይቻላል። ለዚያ ነው “ድርድሩ” ጆሮ ያጣው። ዞሮ ዞሮ ኢሕአዴግ “ድርድሩን” ሲጠራ በተነሳበት ዓላማ ሊጠናቀቅ ተዳርሷል። የምርጫ ስርዓቱን ማሻሻል። ኢሕአዴግ ውጤቱን “በድርድር” የተገኘ ለማስመሰል ስለፈለገ እንጂ ቀድሞውንም ስርዓቱን ለማሻሻል ወስኗል። ለምን እና እንዴት?

፩) ቀዳሚ አሳላፊ (First Past The Post /FPTP) የተባለው የአሁኑ ስርዓት ድምፅ አባካኝ ነው። ነገሩን በምሳሌ ለማስረዳት የምርጫ 2002 የአዲስ አበባ ውጤትን እናመጣለን። በወቅቱ ከመረጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ውስጥ 54% ኢሕአዴግን መረጡ፣ 37% መድረክን መረጡ፣ 9% ሌሎች ተቃዋሚዎችን መረጡ። ነገር ግን ከአንድ ተቃዋሚ በስተቀር ፓርላማ ባለመግባቱ በጥቅሉ የ46% የአዲስ አበባ መራጮች ድምፅ ባክኖ ቀርቷል።

፪) ብዙ መራጭ ባላቸው የምርጫ ክልሎች ብዙ ድምፅ ያገኙ ተወዳዳሪዎች ሲወድቁ፣ ትንሽ መራጭ ባለባቸው የምርጫ ክልሎች ያሉ ተወዳዳሪዎች ባነሰ ድምፅ አልፈዋል። ለምሳሌ በዚያው የ2002 ምርጫ ወቅት በአንድ የምርጫ ክልል 42,555 ድምፅ ያገኙት የመድረክ ተወዳዳሪ አቶ ዑርጌሳ ዋኬኔ ፓርላማ አልገቡም፤ ነገር ግን በሌላ ምርጫ ክልል 12,753 ድምፅ ያገኙት የኢሕአዴግ ተወዳዳሪ ዶ/ር እልፍነሽ ኃይሌ ፓርላማ ገብተው ነበር።

፫) የምርጫ ስርዓቱ ተመጣጣኝ ውክልና (proportional representation /PR/) ቢሆን ኖሮ ለአዲስ አበባ ከተተዉት 23 የምክር ቤት ወንበሮች ውስጥ 12ቱ በኢሕአዴግ፣ 9ኙ በመድረክ እና ቀሪዎቹ ሁለቱ ለሌሎች ተቃዋሚዎች ይሔዱ ነበር። (በዚያው በ2002ቱ ምርጫ)

ይሔ ቅሬታ ሲነሳ ሰንብቶ ነበር። ኢሕአዴግ ግን ባለፉት ሁለት ምርጫዎች ወቅት ባገኘው ድምፅ መሠረት ስርዓቱ ተመጣጣኝ ውክልና ቢሆንም ኖሮ ማለፉ አይቀርም ነበር። ምክንያቱም፣

ሀ) ከምርጫ 97 ወዲህ መራጩ ሕዝብ በምርጫው ስርዓት ዴሞክራሲያዊነት ተስፋ ቆርጧል። ለመምረጥ የሚሔዱትም ወይ የቀበሌ ባለሥልጣናትን የሚፈሩ ተቃዋሚዎች፣ ወይም የኢሕአዴግ ደጋፊዎች፣ ወይም ጥቂት በምርጫ ፖለቲካ መቁረጥ ያቃታቸው መራጮች ብቻ ናቸው።

ለ) ኢሕአዴግ ምርጫው አንድ ዓመት ሲቀረው ገለልተኛ ሚዲያዎችን ከበፊቱ የበለጠ በማፈን ወይም በማገድ፣ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችን በማሰር፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በመሰንጠቅ እና የመንግሥት ሚድያዎችን እና የመንግሥት ተቋማትን ለቅስቀሳ በመጠቀም ራሱን ብቸኛ ተወዳዳሪ አድርጎ ያቀርባል።

ሐ) ኢሕአዴግ ለታይታ ያክል ተቃዋሚ የፓርላማ አባል እንዲኖረው ቢፈልግም፣ በየምርጫ ክልሎች የሚያሠማራቸው ካድሬዎች በሙሉ በኋላ ላይ ላለመገምገም ሲሉ በራሳቸውን የምርጫ ክልል ኢሕአዴግን አሸናፊ ለማድረግ የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው ዘዴ ተጠቅመው ያሸንፋሉ። 100% ውጤት የተገኘው በነዚህ ተንኮሎች እና ዘዴዎች ነው።

ስለዚህ (ሐ) ላይ የተጠቀሰው ችግር ሳይፈጠር (ካድሬዎቹ አሉታዊ ግምገማ ሳይቀርብባቸው) ተቃዋሚ ፓርላማ የማስገቢያው መንገድ የ”ተመጣጣኝ ውክልና” በመጠቀም መሆኑን ኢሕአዴግ ተረድቷል። ነገር ግን ደግሞ ድንገት የምርጫ 97 ዓይነት ነገር ተከስቶ በቀላል የተቃዋሚዎች ዳግማዊ መነቃቃት በተመጣጣኝ ውክልና የሚገኘው ውጤት የተቃዋሚዎቹን ድምፅ ድምር ከኢሕአዴግ ሊያስበልጠው እንደሚችል ያውቃል። ለዚህ ነው “ቅይጥ ትይዩ” (Mixed-Parallel) የሚባል የስርዓት ማሻሻያ ይዞ የመጣው።

በጣም የሚያሳዝነው ተቃዋሚዎች “ቅይጥ ትይዩ” የተባለው የምርጫ ስርዓት ምን ዓይነት እንደሆነ አለማወቃቸው ብቻ ሳይሆን፣ ኢሕአዴግ እንዲያስረዳቸው መጠየቃቸውም ጭምር ነው።

በተመጣጣኝ ውክልና ስርዓት ከግል ተወዳዳሪዎች ውጪ ፓርቲዎችን ወክለው የሚቀርቡ ግለሰቦች አይኖሩም። ፓርቲዎቹ ባገኙት ውጤት ልክ ነው ለወንበሮቹ ሰው የሚመድቡት። ቅይጥ ትይዩ የተባለው ስርዓት የተወሰኑ ወንበሮች በቅድሚያ አላፊ ስርዓት፣ የተወሰኑ ወንበሮች ደግሞ በተመጣጣኝ ውክልና የሚገኝበት እና ሁለቱንም የምርጫ ስርዓቶች ጎን ለጎን ማስኬድ የሚቻልበት ስርዓት ነው። ይህ የምርጫ ስርዓት አንድ ፓርቲ ለረዥም ዓመታት የገዛባቸው አገሮች የተከተሉት ስርዓት ነው። በተለይ የምርጫ ክልሎቹን በደጋፊዎቹ አሰፋፈር ማወቀር (gerrymandering) የቻለ ፓርቲ ዘላለም አሸናፊ  የሚሆንበት ስርዓት ነው።

ተቃዋሚዎቹ ስለተጠቆመው የምርጫ ስርዓት ኢሕአዴግ ካብራራላቸው በኋላ ነው “መደራደራቸውን” የቀጠሉት። አሁን 11 ፓርቲዎችን ያቀፈው ቡድን 60:40 (ማለትም 60% ቀዳሚ የሚያልፍበት፣ 40% ተመጣጣኝ ውክልና) እንዲሆን “የመደራደሪያ” ምጥጥን በማቅረብ “ቅይጥ ትይዩ” ስርዓትን ተቀብለዋል።

በበኩሌ፣ ትክክለኛው “ሕዝባዊ ስርዓት” የሚለካው በምርጫው ውጤት ሳይሆን በምርጫዎች መካከል ባለው ሕዝባዊ ተሳትፎ ነው ብዬ ነው የማምነው። ይህ ደግሞ ያለ ሲቪል ማኅበራት፣ ያለ ገለልተኛ ብዙኃን መገናኛና ለሕዝብ ወገንተኛ የሆኑ ተቋማት በሌሉበት ይሳካል ብዬ አላምንም። ሆኖም፣ የምርጫ ስርዓቱም ቀላል ቁም ነገር ነው ብዬ አላስብም። ስለዚህ፣ ለእንደኛ ዓይነቱ አገር ድምፅ አባካኙ ቀድሞ አላፊ ስርዓት አዋጭ ነው ብዬ አላምንም። የተሻለው ተመጣጣኝ ውክልና ነበር። ይህ ግን ቀድሞም የይስሙላ በተባለው ድርድር፣ በፓርቲዎች አላዋቂነት ሳቢያ የማይሆን ሆኗል። ኢሕአዴግ በራሱ ፍላጎት የጀመረውን ድርድር እንደፍላጎቱ እየጨረሰው ነው።


[WARNING: If a personal note bores you, don’t read this.]
I was 11 years old boy when EPRDF took power. As a kid, I had a confused feeling during the time the then ‘Woyane’ controlled Addis on Ginbot 20. During the nights before, we used to listen to ‘Dimtsi Woyane’, radio broadcasted by TPLF from battlefield. I remember the elderlies were very worried however I kind of loved the guys from what they, the Woyanes, spoke on the radio. In addition, my father, despite being a member of the then national guard in the Ethio-Somali border, had said he had wished ‘Derg’ to be defeated, or at least my sister had told me he had said so. Derg’s defeat wasn’t just my father’s dream come true for me. He also retired and reunited with his family.
Even though the ‘Woyanes’ were portrayed like monsters by the time they took control of Addis Ababa, I liked them. I stared at them wondering at their never cut hair, old shorts and sandals. I told a couple of them that ‘I love them’ when they come to our village for disarmament and search for illegal holds of arms.
Soon later, they are worn with good uniforms, and ‘kesikis’ shoes which I had wished to have a pair. Their name became popularly EPRDF and the ‘Woyane’ turned a derogatory term for ‘Derg’ propagandists already associated it with equivalence to ‘separatists’.
EPRDF took control of state owned and widely listened only radio station and preached a lot about democracy, national liberation, equal rights and so on. It was my formative age. Everything I listened to was sweet and persuasive. In contrary, the elderlies in our neighborhood became so critical of the new regime. I didn’t know why but I thought it was only because it is a government that EPRDF is hated and that only because newly formed opposition political parties are not given the governing chance, that they are preferred.
I didn’t know why people became more concerned about their ethnic background. Discussions of the older people seemed always as if there is something to be worried. I couldn’t get the slightest idea of what bothered them until I turned 18 and went with my father to ‘Kebele’ to get an ID. I was asked what my ‘nationality’ (not citizenship) was. I never felt belonging to any ethnic group before. I turned my face toward my father who took almost a minute to respond to. He looked like he lost an internal battle immediately after that. My mother and father are from different regions and it never mattered before. Until now, telling the ‘nationality’ written on my ID is embarrassing to me. I always felt it isn’t representative of my identity. It is like I’m legally forced to feel belonged to one group and not to the rest.

I’m from a very humble background, economically speaking. Some sort of bitterness source of which I didn’t figure out started growing in me against the regime of EPRDF. I worked as a day laborer (‘Gutter maintainer’) when I finished high school. It was when Addis started to boom in construction. I have witnessed buildings and real estates mushrooming. These real estates’ residents lifestyle comparison to the livelihoods in my neighborhood was significantly clear. Then, I stopped working there and joined college. I had needed pocket money and started home tutoring young adults of well to do families. I graduated from college and formed a cooperative association with my college mates. Even though, cooperatives were encouraged by the time we were founding that association, many doors in the offices of the ‘kebeles’ were closed to us because we were not involved as member of any league whose members the regime wants to promote.
It was no surprise that when I first become politically active that my most concerns were of economical. I worry about the ever growing economical gap, the corruption and the marketing system that is over controlled by the regime. Now, years later, these are the least of my worries. It is not because they are improving. They are even worsening. However, by the time I had to thrive, survival became the issue again as I became more endangered beyond my wishes for economic betterment.
Back in the most contested election of 2005, I have supported CUD, participated in its unforgettable mass demonstration in May 2005, voted for it, protested in streets when I believed the election was rigged. But, I never thought EPRDF was collection of people who will let us pay a lot, afterwards, as people for staying in power. In the post 2005 election anti-government protests, the regime’s forces killed my age-mate neighbor Lealem. The regime has made everything difficult to all of hardworking age-mates of mine in the poverty wrecked neighborhood, Ferensay Legasion.
With all the challenges I have faced and the efforts I have done, life isn’t any more difficult to survive but everything in it is meaningless. The family and families in the neighborhood that have raised me are still in that vicious cycle to survive in the poverty that I had grown in. The state rhetoric of economic growth couldn’t be convincing. The construction boom in my city feels like the wealth of the city belongs to someone else. I reflected only a few of my feelings in multiple blogs I have written.
Blogging has helped me think, revise my stances, rethink the sources of problems and engage in more than writing activities. Through blogging, I have come a long way. I’m a person with a developed or even maybe with a different ideology than the person who I was when I started blogging.
My bold activities, including blogging, against the regime’s officials’ impunity, its failing policies and unconstitutional acts cost me a lot already. Everything became personal but again, I did downplay it as if it is not personal. I was detained, tortured and charged with “terrorism” and held in prison for 544 days to finally get acquitted and forced to defend myself of downgraded charges of ‘inciting violence through writing’. The case is still on hearing in two courts: at the Federal High Court in defense of the downgraded charge and at the Supreme court with my colleagues because the Federal prosecutor appealed against our acquittal. To appear before two courts for a single case is against the procedural law of the country.
Life after imprisonment couldn’t be the same as before for my colleagues and myself. I have lost all the trust on the government’s either capacity or willingness to protect its people’s wellbeing. I have read a lot of government sponsored lies written on state-owned Addis Zemen newspaper against the Zone 9 blogging collective to which I am a co-founding member and to which we were targeted of ‘enemies of the government’. My friends and I are living a tragedy. We can’t be anywhere we want for we don’t have the luxury of being considered commoners, but dissidents from whom the government is looking a mistake to throw back to jail.
Some people tell me the countless migration of Ethiopians at risky routes is motivated by economic challenges; I say the economic challenge is the foster child of political failures. The same kind of people tell me prisoners were killed when they try to escape a prison that had caught fire; they also tell me people died in stampede during a protest in a religious festival where government in the country fired tear gas. I disagree because the cause of deaths in either incident is irresponsible acts of government forces. I don’t just blame the helpless victims. The attempt to justify such kind of things drives me emotionally mad. It drives me mad because it could have been me who has drowned in an ocean or who got executed by some terrorists in Sahara desert; it could have been me who has been burned down into ashes or who has been killed in the stampede. I feel the pain because I know it all comes to me yet before a while. And, I don’t hate (even like) my emotionality because it is what makes me human.
I get angry, then sad, then frightened. I became more vulnerable than before and more than an average person. This is the life of mine and my friends. We were raised in a way to end up dissidents. We are emotionally affected. In fact, we can’t have humanity without being emotional.

Now, the government in Ethiopia has declared a ‘state of emergency’ that lasts in six months. As ‘the usual suspects’ because of our dissents, my friends and I are scared more than before. It has always been a risky thing to criticize the government here. Furthermore, this declaration has given the government the right to arrest us even without an excuse. I’m publishing this personal note as a blog because I am afraid I may be arrested sometime soon. If so I want people read me and understand me. I want people to also understand my likes to understand the desperate protests in Ethiopia. It’s an attempt to survive as human with dignity.

How many prisoners of conscience do you think are held in Qilinto, Kality, Shoa Robit and Zeway Federal prisons for having different political thoughts to the regime in Ethiopia? In Qilinto alone, there are estimated of 500 of them who are not convicted yet. How many of these are recognized by the public to whom they are sacrificing?

My arrest and 18 months of stay in prison has helped me meet a lot of prisoners. I met a guy who has never heard the name of a rebel group (Amhara Democratic Forces Movement) of which he was accused being a member; I met a guy who is accused for affiliation of Oromo Liberation Front whose leaders he can’t name; I met the ex-president of regional state of Gambella, Air Force Capitans, and many others who has no one to visit, hire a lawyer, or even to remember to… By the time I was held in Qilinto, many Ethiopians who raised religious freedom from State interference, Gondere Amharas, Oromo University students, youths from Gambella and Benishangul Gumuz, Tigrians who were suspected for having affiliation to the Tigrian rebel group, and many Ethiopian Somalis were held there. Many of these share the same cahllenge: they have no one to give the least recognition why they were jailed. I used to deliberately avoid hearing stories of these inmates while I was there to avoid the feeling that I can’t do any good for them. After my release, the feeling haunts me in different form. I sometimes ask myself if I might feel better jailed than to helplessly do nothing as a ‘free man’.

A week before the wake of Ethiopian new year, Qilinto prison caught in fire. Guards shot many prisoners dead when they try to escape the fire. Now, the survivors are distributed to other prisons, Shoa Robit and Zeway, while a few others are left to stay in a undamaged zone in Qilinto. The prisoners who are moved to other prisons had no shoes (were barefooted) and have no clothes to change. Those who have regular visitos are now given with pair of slippers and cloths to change, but most political prisoners whose family members and friends are in remote rural areas are still on barefoot. Even worse, no one knew which one of them did make it alive from the blaze for they have no one who speaks about what had happened to them. (Prison admins claimed the dead are 23 but informal reports indicate more than 70 prisoners are missing.)

If you ask me how many of these 500 political prisoners in Qilinto have actually committed a crime, my answer would be ‘maybe ten’. One way or another, all of them are victims for trying what they thought would bring better change for their people. They are people who care.

These prisoners of conscience are not all well known. They do not have family and friends support. Most of them are from remote rural areas. Some of them were breadwinners for their families before their arrest and they don’t know the fate of their respective families after they are jailed. In addition to this and physical and psychological abuses in prison, they also have to face a lot of challenges:

1. They don’t have basic necessities (such as clothes to change, blankets, pyjamas, towels…) nor pocket money to buys some things such as cleaning detergents, toothbrushes and toothpastes, or even to have a cup of coffee once a week. However, there are a few job opportunities for prisoners, they are not allowed for political priosners.

2. They miss someone who talk to them. Most of the political prisoners have no one visiting them regularly. Even though they do have many inmates, none of them can replace the feeling visitors give a prisonor.

3. They need information. They want to know what is going on in the country. They don’t have any reliable source of information other than windfall rumors and EBC’s state-led biased reports. They need to update themselves with contemporary realities.

These are all mere wishes to many of the political priosners.

The way we support the political prisoners has a direct implication for those who are trying their best to make a change in the country. They will either be encouraged for they will have our support in case they fall victims of the regime or not. This is why we need to ask what we can do.

Currently, it is only a few concerned citizens who are visiting and trying to help political prisoners at regular basis. This has made the burden on these people very much. What if each of us try to do what we can? What if those of us who have the time select a political prisoner and keep visiting her/him regularly? What if those of us who have the money keep contributing some regularly? Wouldn’t this be a great deal of care and promise for those who are sacrificing for a better world?

ሐምሌ 2006 ከማዕከላዊ ወደ ቂሊንጦ ስዛወር፣ ዞን ሁለት ነበር የተመደብኩት። በወቅቱ በሽብር የተከሰሱ ብዙ ጎንደሬዎች ነበሩ። አልጋው ሥር “ደቦቃ” በማስተኛት ያስተናገደኝም ቢራራ የተባለ ጎንደሬ ነበር። ከዚያ በፊት ከሥሙ በስተቀር የማላውቀውን ፋሲል ደሞዝን አንድ ዘፈን ያስተዋወቀኝ እሱ ነው። ዘፈኑን እስከዛሬ ባልሰማውም ሁለቱን ስንኞች ግን በቃሌ ይዣቸዋለሁ። “አረሱትን አልሰማኸውም?” አለኝ ድጋሚ ‘አልሰማሁትም’ አልኩት ባለማወቄ ሲገረም አይቼ እያፈርኩ፤ ስንኞቹን ነገረኝ።

“አረሱት ይሉኛል የመተማን መሬት፣
ያውም የኛን ዕጣ
እነሱ ምን ያርጉ ከኛ ሰው ሲታጣ።”

ሰሞኑን 17 ያህል አርቲስቶች ለአዲስ ዓመት ዋዜማ አቅደውት የነበረውን የሙዚቃ ድግስ በሐዘናችን ምክንያት መሰረዛቸውን ሰማሁ። አርቲስቶቻችን ሰው እየወጣቸው ነው ማለት ነው የሚል ስሜት ተሰማኝ። እኛው ያከበርናቸው አርቲስቶች የሕዝባችንን ሐዘን ማክበር ከጀመሩ ትግላችንንም የሚቀላቀሉበት ግዜ ሩቅ አይሆንም፣ እኛም ‘አርቲስት’ የሚለውን ቃል ስድብ ከማድረግ እንቆጠባለን እያልኩ ሳስብ ሳልሰማቸው ያመለጡኝ ብዙ የትግል ዘፈኖች እንዳሉ ተረዳሁ።

የኦሮምኛ ዘፋኞች ዘፈንን የትግል መሣሪያ ማድረግ ከጀመሩ ሰንበትበት ብለዋል። ሁሉም ዕኩል መደመጥ አልቻሉም እንጂ ባለፈው አንድ ዓመት በአማካይ በቀን አንድ የትግል ዘፈን እየለቀቁ ነበር። ከሁሉም ግን በጣም ተወዳጅ የሆነውና ቋንቋውን የማታውቁትን ሳይቀር የሚወዘውዘው የሀጫሉ ‘ማለን ጅራ’ ነበር፤ ስለዚህ ዘፈንም መጀመሪያ የሰማሁት እዚያው ቂሊንጦ በመጣ ወሬ ነው።

ኪነ ጥበብ ትግሉን ሲቀላቀል የትግሉን መብሰል የሚያሳይ ምልክት አድርጌ ነው የማየው። በአዲስ አበባ መንግሥትን በገደምዳሜ የሚወርፉ ትያትሮች ከሌሎቹ የበለጠ ብዙ ተመልካች አላቸው፣ የመግቢያ ዋጋቸውም ውድ ነው። ምክንያቱም የሕዝቡን ዝምታ ይናገራሉና። አሁንም፣ አርቲስቶቻችን የትግል ዘፈኖችን ሲዘፍኑ በሕዝብ ልብ ውስጥ ያላቸው ዋጋ ይጨምራል።

ስለፋሲል ደሞዝ እነዚያ ስንኞች ሳወራ ወንድሜ “‹እንቆቅልሽ› የሚለውን አታውቀውም?” አለኝ። አላውቀውም ነበር። ይገርማል ፋሲልን ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህ ዘፈኑ ሰማሁት፣ አየሁት። ክሊፑ ላይ፣ ሴቲቱ እንቆቅልሽ ትጠይቀውና መልሱን ባለማወቁ “አገር ስጠኝ” ትለዋለች፣ እሱ ግን እንዲህ ይላታል።

“እንቆቅልሽ፣
በሰም ለበስ ቅኔ፣
አሁን ገና፣ መጣሽብኝ ባይኔ።”

ፋሲል “በይ ደስም አላልሽኝ ጨዋታ ቀይሪ” እያለ ሲያንጎራጉር የሆነ ልብን የሚኮረኩር ኃይል አለው። ወንድሜ “ይሄ ይገርምሃል እንዴ?” አለኝና የይሁኔ በላይ አዲሱን ዘፈን አስደመጠኝ። ለወትሮው፣ ይሁኔን ከፍቼ የማዳምጠው ዘፋኝ አልነበረም። ይሄንን ‘ሰከን’ የሚለውን ዘፈኑን ስሰማው ግን የማላውቀው ስሜት ልቤን አተራመሰው።

“…ሰከን በል፣
ሰከን ማለት፣
ነው ጨዋነት
ሰከን ማለት፣
ነው ጀግንነት
ወታደሩ፣ ሰከን በል
አፈሙዙን ሰከን አርገው፣
ቃታህንም እንዳትስበው፣
ባዶ እጁን ነው፣ የሚጮኸው፣
ሠላማዊ፣ ወንድምህ ነው፣
ሰከን በሉ፣ ሕዝቤን ተዉት
ድምፁን ስሙት፣ አትግደሉት…”

በማለት የመንግሥትን ሀጢያት “…ውጉዝ ከመአርዮስ” ብሎ በማውገዝ፣ ስለኅብረት ሲባል፣ “በወላጁ ጥፋት፣ አይወቀስ ልጁ” እያለ መስከንን ይመክራል።

ናቲ ማን ቀጠለ። ናቲ ደግሞ በኦሮምኛ ስልተ ምት “አሁን ተነካሁ” እያለ፣ እሽክም፣ እሽክም አስባለኝ።

“ኦሮሞን፣ ኦሮሞን ሲከፋው
አሁን ተነካሁ
አማራን፣ አማራን ሲከፋው
አሁን ተነካሁ…”

ከዚያ ደግሞ የመስፍን በቀለ ዜማ ቀጠለ። በቀረርቶ የሚጀምረው የመስፍን “ሠላም ለኢትዮጵያ” አዲስ ትውልድ መጥቷል ይላል። ወራደሩንም እንዲህ ይለዋል፦

“ወታደሩ ጓዴ፣ አንተ ያገሬ ሰው፣
ወንድምክን አትግደል፣ ብረትክን መልሰው።…”

ሌንሴ ለሜሳ ደግሞ ጆሮ በሚለሰልስ ድምፅዋ፣ “ተነቃንቋል” ትላለች፣

“ተነቃንቋል ጥርሱ ይነቀል፣
ይነቀል፣
ይነቀል ይውለቅ
የአሉላ የጆቴን ትከሉበት ወርቅ፣
ክፍተቱ እንዲሞላ ውበቱ እንዲደምቅ።…”

መክፈቻዬ ላይ የጠቀስኩትን ፋሲል ደሞዝን መዝጊያም ላድርገው። በቅርቡ በለቀቀው ዘፈኑ እንዲህ ይላል፣

“…ኧረግ ወዲያልኝ (ወዲያልኝ)
ኧረግ ወዲያልኝ (ወዲያልኝ)
በቃ ሒድልኝ (ሒድልኝ)
25 ዓመት አላገጥክብኝ።…”

ክብር ለእነዚህ አርቲስቶች ይሁን!
አሜን።

Some Facebook friends are recently tagging me with their posts of ‘solutions’ to the contemporary crisis in Ethiopia. (i.e. the anti-government protests in Oromia and Amhara, two biggest regions in Ethiopia). Most of these Facebook friends recommend maintenance or what’s otherwise called ‘cosmetic change’ to the regime. Others seem to be conspirators against the ‘unprecedented’ cooperation of biggest players in Ethiopian politics, the Oromo and Amhara people, against the ruling Tigrian elites group, TPLF.  (The group claims to represent 6% of Ethiopian people (Tigrians) as compared to 62% – Amhara + Oromo people). The latter (of facebook friends suggesting solutions) claimed that it is only Oromo Protests that’s genuine and some went far to portraying Amhara protests as an act of power mongering.
There is no Half Liberty!
In my opinion, it is hardly possible to give one sect of a society its freedom and denying the rest. Freedom will either be assured for all or is denied for all. One of the nations in Ethiopia cannot be given regional autonomy and proportional representation in the federation while others are denied these. It will be oppressed with the rest, or get freedom with them. Even TPLF (which is the supreme Front in the coalition of four parties in the name of EPRDF) including its makers and supporters will only get liberated or be free when it lets others free. The common understanding that a jailer is not free until it frees its prisoners is true. One has to free their prisoners to regain their freedom of movement; otherwise, they will have to be sitting there watching their victims. 
So What to Do?
The solution should be all inclusive. But this happens only if all of us have the genuine intention to compromise on our interests for the sake of justice, fairness and peace. Now, all the power and opportunity is controlled by the ruling party, EPRDF. So, EPRDF must be the sole body willing for this to be true. The issue is freeing the party itself as well as its dissent. Otherwise, however its oppression increases, the public grievance and riot will also increase and the challenge that can be solved through compromise today may not tomorrow. 
In this, maybe naïve, understanding of mine that EPRDF may become willing to hear alternative solutions, I suggest a filtered compilation of alternative solutions from what I heard of people’s recommendations.

1) Apology
Ethiopian people deserve an apology. TPLF/EPRDF should ask the Ethiopian people an apology for all the mistakes and wrong doings that it has done from its conception up until today and even for leading the country to a dangerous end. This has to be done in a written format.
2) Amnesty and Warranty 
We have to cross the bridge of past failures at some point. EPRDF should give amnesty and release all people who were convicted and are on hearings of court proceedings in relation to their political stance. The amnesty should not be with any pre- & post-conditions. In addition, the ruling group should cancel the proclamation that labelled dissent organizations as ‘terrorists’;  it should give warranty for the return of exiled politicians, journalists and activists so that they would be able to contribute for the political fate of their country. Rebel groups should also be given the guarantee to peacefully and legally act according to their political program. A proclamation of amnesty and warranty should be passed by the parliament as to this end. 
3) Discourse
Anti-terrorism proclamation, the charity law and the press laws inacted in the country are used to restrict democratic discourse. Therefore, they should be cancelled for the time being until a legitemate house ratifies other ones (or until it amends them in a way) that don’t stifle constitutional rights. In the mean time, successive and multiple country-wide dialogue that are broadcasted live in the state-owened television with the participation of all stake holders and with moderation of international rights groups should be conducted.  
4) Election
Finally, by freezing the current parliament including the electoral board and by establishing a temporary electoral board of technocrats from other independent countries, there should a new election to be launched at ‘national’ and regional level.
Having suggested that, I have also considered possible criticisms for these alternative solutions:
A) These don’t consider TPLF’s position not to ever compromise;
B) A naïve comment that has assumed the recent protests have shakendown EPRDF’s hold;
C) A solution that encourages dependency on foreign support;
D)  A comment that disregarded the immediate necessity of resolving the controversial issues regarding federal structure, electoral system, Parliament system, land ownership and others in the constitution.
Regarding the first two possible comments (put in ‘A’ & ‘B’), it is because I have the fear that the crisis we are in go worse than better that I wanted to take the risk of being ignored speaking rather than keeping quite. On the other hand, I suggested the participation of independent foriegn technocrats and rights groups because they are the only possible bodies who wouldn’t have much interest to rig the election for transition. My answer for the possible criticism put in ‘D’ is my enthusiasm that if we once established a legitimate house of representatives, the rest would be taken care of by them. Controversial issues will always be there. But, in the way down the road from there, everything to reform including constitutional ammendments is possible for it is easy to do so once a platform is lay for democracy. The most urgent and important issue, for me, now is forming a legitimate government for the majority.

“Sport is a profession that needs discipline,” Haile Gebresilasie told to one FM radio sports show in Addis. Haile Gebresilasie is the most known and successful Ethiopian athlete who has broken more than three dozens of records from 1,500 meters to marathon races. He said “Athletic federation should not be ruled by people who are politically assigned; if we’re continuing in the same manner, the worst is yet to come.” He was talking about the fact that Ethiopia’s scores at the Rio Olympic have declined as compared to previous Olympic Games. The Ethiopian Olympic Committee had planned to bring at least 4 Gold, 4 Silver and 4 Bronze medals in Rio Olympic 2016 where it has returned with only eight medals: 1 Gold, 2 Silver and 5 Bronze medals standing far behind its usual competitor team Kenya.
‘Robel The Whale’ – the Symbol for Nepotism
Ethiopia had begun its participation in Rio Olympic in an ever embarrassing 100 meters free style swimming race. Robel Kiros is the son of the President for Ethiopian Swimming Sport Federation. Robel went to Rio with his father. According to Addis Admass, a weekly Amharic newspaper, there were claims that his coach was not allowed to go to Rio with Robel because the budget allocated for the Olympic is used by his father. Robel finished the race 59th out of 59 participants and he finished it 17 seconds later to the pacesetter. His body wasn’t athletic at all and Ethiopian social media sphere was hit by criticism over his defeat and in question how he could make it to there.
The annoying fact is that Robel’s father is from Tigray, a region with 6% of Ethiopian population, from where the ruling group has emerged out. People took this as an act of nepotism not just because Kiros Habte (Robel’s Father) is from Tigray but also because all nine Ethiopia’s sports federations presidents are Tigrians. In the federal government of Ethiopia, most powerful positions are taken by Tigrians who are TPLF members and it was easy for everyone to easily take Robel’s embarrassing defeat at the Rio and his unprecedented participation as symbol to the nepotism widespread in the country.
Feyisa Lilesa – the Heroic Symbol for Public Protests
Ethiopia’s last participation in Rio was in men’s marathon race on which Feyisa Lilesa gave the world another but different experience than ‘Robel the whale’ had given. A husband and father for two, Feyisa Lilesa, has become silver medalist in Rio Marathon Men Race. Feyisa, upon crossing the finishing line of the race (and later when he sat for press conference), has displayed a political protest by crossing his arms up in a symbolic way Ethiopian political protesters use to show that they are not free.
Feyisa, unlike Robel, is from Oromia, the biggest and most populous region in Ethiopia’s federation. Oromo people have been protesting for at least the past 10 months continuously over injustices and marginalisation while losing more than 600 lives during brutal attempts of police to crackdown the protests. Feyisa, like Robel, has become a hot agenda in Ethiopian social media community but, again unlike Robel, it was with joy and admiration that everybody was referring to him. 
From Robel To Feyisa
Robel is a privileged loser where as Feyisa is the un-favored winner. Robel is coming back to his country however it is too risky for Feyisa to enter the country. Feyisa himself said to journalists at Rio, “if not kill me, they will send me to prisons”. Robel vowed that he will participate in a better condition in the next Olympic Games to be held in 2020 in Tokyo. This seems unlikely for Feyisa. By gesturing political protest, Feyisa put his career at risk. He might face sanctions from International Olympic Committee for showing prohibited political gesture during the game.
On the other hand, Robel remains a hated symbol of nepotism in Ethiopia whereas Feyisa is already portraid as the son of his people. Feyisa may become Stateless or end up refugee in another country; and/or he may be revoked from the medalists list where he finished second; but, he will always remain the symbol of defiance at the hearts of concerned Ethiopians.

በበፍቃዱ ኃይሉ

ዓይን የሚፈታተን ደብዛዛ ብርሃን ያለበት ክፍል ውስጥ አስገብተው ከኋላዬ ወፍራሙን የብረት በር፣ ልብ በሚያደባልቅ ጓጓታ ድብልቅ አድርገው ዘጉት፡፡ ወደመታሰሪያ ክፍል የገባሁት እንዲህ ነበር፡፡ ሰዓቱ ከምሽቱ 3፡00 ወይም 4፡00 ሰዐት ገደማ ነው፣ ሚያዝያ 17፣ 2006፡፡ ከውስጥ መሬት ላይ የተኙ ሰዎች ይታዩኛል፡፡ በእጄ ያንጠለጠልኩትን ፌስታል እንደያዝኩ ተራ በተራ አየኋቸው፡፡ አንደኛው ከተኛበት ተነስቶ ቁጢጥ አለ፡፡ ‹ካቦው ይሄንኛው ነው ማለት ነው› አልኩ በልቤ፡፡ ‹የሻማ ሲጠይቁኝ ኪሴ ውስጥ ያለውን ሁሉ ሰጥቼ ለመገላገል ፈልጌያለሁ› እነርሱ ግን የሻማ አልጠየቁኝም፡፡ ‹አረፍ በል› አሉኝ፡፡ ጠርዝ ላይ ተቀመጥኩ፡፡ ‹ራት በልተሃል?› አሉኝ፤ ‹አዎ በልቻለሁ›፡፡

‹ምን አድርገህ ነው?›
‹ጸሐፊ ነኝ፡፡›
‹አሃ፣ ጋዜጠኛ ነህ?›
‹አይ፣ ኢንተርኔት ላይ ነው የምጽፈው፡፡›
‹ሙስሊም ነህ?›
‹አይ አይደለሁም፡፡›

የሚያስፈራ ዝምታ ሰፈነ፡፡ ‹እናንተስ?› አልኳቸው፤ ዝምታውን ለመስበር፡፡

ቁጢጥ ያለው፣ ‹እኔ እና እሱ› አለ ወደ አንደኛው ልጅ እየጠቆሙ ‹በሙስሊሞች ጉዳይ ነው፤ እነሱ› አለኝ ወደሌሎች ሦስት ልጆች እየጠቆመ ‹ከጋምቤላ ነው የመጡት፤ እኚህ ከሶማሊ ክልል ነው የመጡት፡፡ ያኛው› ወደጥግ ወዳለው እየጠቆመ ‹በግንቦት ሰባት ነው የተጠረጠረው› አለኝ፡፡ ሰባት ነበሩ፡፡ እኔ ስምንተኛ ሆንኩላቸው፡፡ በሳይቤሪያ የዘጠኝ ቁጥር እስረኛ ሆኜ ተቀላቀልኳቸው፡፡ ማብራሪያውን የሰጠኝ ረደላ ሸፋ ነበር፡፡ ሦስቱ አኙዋኮች ኡማን ኝኬው፣ ኡጁሉ ቻም እና ኝጎ ኩምቻሬ ነበሩ፡፡ ሶማሌው፣ እኔ በገባሁ በሁለተኛው ቀን ስለተፈታ ዘነጋሁት፡፡ የረደላ አባሪ ሐሰን ነው፡፡ ጥግ ላይ የነበረውና በክፍላችን ብቸኛው የግንቦት ሰባት ወታደርነት ተጠርጣሪ የነበረው አበበ ካሴ ነበር፡፡

ኒጎ ኩምቻሬ እሱ ተኝቶባት የነበረውን ፍራሽ ለቆልኝ እስከመጨረሻ ድረስ የቆየሁባትን ጥግ ላይ ያለች ምቹ ቦታ አወረሰኝ፡፡ ‹በቃ፣ አሁን ተኛ እና ነገ እናወራለን› አሉኝ፡፡ እሺ አልኳቸው፡፡ እነርሱ ተኙ፡፡

አበበ ካሴ እኔ በገባሁበት ሰዐት ምርመራ ጨርሶ ነበር፡፡ ነገር ግን በአስፈሪ ዝምታ የተዋጠ ሰው ነበር፡፡ ተሰብስበን ኮንከር (ካርታ) ስንጫወት ብቻ፣ እየዳኘ በተራው ይጫወታል፡፡ እየቆየን ስንመጣ ግን ቀስ በቀስ ያዋራኝ ጀመር፡፡ ጠርጣራ ስለነበር፣ ድምፁን በጣም ዝቅ አድርጎ በእርጋታ ነበር የሚያዋራኝ፡፡ ምርመራ አምሽቼ ስመጣ፣ እልሄን የምወጣው እነሱ ጋር ነበር፡፡ ያሉኝን ብስጭቶችና ብሶቶች ሁሉ እነርሱ ላይ እዘረግፈዋለሁ፡፡ እነርሱም፣ አብዛኞቹ ምርመራቸውን ጨርሰው ክስ የሚጠባበቁ ስለነበሩ፣ እኔን ከበው ማፅናናት ብቻ ሆነ ሥራቸው፡፡ አበበ አንድ ቀን ማታ መጥቼ እንደለመድኩት ‹ሊገሉኝ ነው፤ ካልገደሉኝ አይለቁኝም› እያልኩ ሳማርር፡፡

‹አሁን ይቺን ተመታሁ ብለህ ነው?› አለኝ፡፡

በአባባሉ ተናድጄ መልስ ከመስጠቴ በፊት የእጆቹን አይበሉባ አሳየኝ፡፡ ‹ጥፍሮቼን እያቸው› አለኝ፡፡ ጥፍሮቹ ጣቶቹ ላይ የሉም፡፡ ‹እኔ እንኳን እንዲህ አድርገውኝ ዋጥ ነው ያደረግኳት፡፡ ወንድ ልጅ ቻል ነው ማድረግ ያለበት፡፡ ወንድ አደለህ እንዴ?› እኔ የወንድነት ጀብድ የምመኝበት ጊዜ ላይ አልነበርኩም፡፡ ይልቁንም እሱ እኔን ለመምከሪያ ያሳየኝ ጣቶቹ ማስፈራሪያ ሆነው አረፉት፡፡ እኔም ባለተራ ነኝ ብዬ አሰብኩ፡፡

አበበ ካሴ ቀድሞ የመከላከያ ሠራዊት አባል የነበረ፣ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት የተዋጋ፣ ከዚያ በኋላ ግን ለቅቆ ግንቦት ሰባትን የተቀላቀለ ወታደር ነበር፡፡ ሲራመድ ያነክሳል፡፡ ‹ምን አርገውህ ነው?› ስለው ‹ምኑን አውቄ› አለኝ፡፡ ሲደበደብ ራሱን ይስት ነበር፡፡ አበበ ካሴ ከኤርትራ ጎንደር የዘመዱን ሠርግ ለመታደም መጥቶ ነው የተያዘው፡፡ በምርመራ ወቅት የግንቦት ሰባት ወታደር መሆኑን በፍፁም አላመነም ነበር፡፡ ያደገበት እና የኖረበት ኩራት በዱላ ፊት መንበርከክ አልፈቀደለትም፡፡ ክስ ከተመሠረተበት በኋላ ግን ለፍርድ ቤቱ “አዎ፣ የግንቦት ሰባት ወታደር ነኝ፤ የሆንኩትም አምኜበት ነው” ብሏል፡፡

አበበ ካሴ ከኔ ክፍል ተቀይሮ ተስፋለም ታስሮበት ወደነበረው 4 ቁጥር የተዛወረው ከአጭር ቀናት በኋላ ነበር፡፡ ነገር ግን መልሰን ቂሊንጦ ዞን ሁለት ተገናኘን፡፡ አበበ መጀመሪያ የተከሰሰው በፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ በአንቀጽ 4 ቢሆንም፣ የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ከተደመጡ በኋላ ተቀይሮለት 7/1 ሆኖለታል፡፡ የዛኔ ‹እንኳን ደስ አለህ› ልለው ክፍሉ ሄጄ ነበር፡፡ ሳቀብኝ፡፡ ‹ታስሬ እያለሁ ቁጥር ተቀነሰልኝ ብዬ የምደሰት ይመስልሃል?› ስሜቱን አላጣሁትም፡፡

እንደአበበ ካሴ በቂሊንጦ አስተዳደር የሚጠላ የፖለቲካ እስረኛ አልገጠመኝም፡፡ አበበ ሕክምና ተከልክሎ እግሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየተሸመቀቀ አጥሮ ግቢ ውስጥ በምርኩዝ ነው የሚንቀሳቀሰው፡፡ ብልቱ ላይ በምርመራ ወቅት በደረሰበት ጉዳት የሚያዥ ነገር ተከስቶበት ሕክምና ሲጠይቅ ተከልክሏል፡፡ በጥቅሉ የሰው ልጅ ላይ የሰው ልጅ ሊያደርስበት የሚችለው በደል ሁሉ እየደረሰበት ነው፡፡
አበበ ካሴ አሁን 7 ዓመት ከዘጠኝ ወር ፅኑ እስራት ተፈርዶበት ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ገብቷል፡፡

እንደ አበበ ሁሉ አዱኛ እና መገርሳም በየቀኑ ሐሳቤ ናቸው፡፡ ማዕከላዊ ሳይቤሪያ የሚባለው ወንዶች ክፍል፤ ዘጠኝ ቁጥር ውስጥ ሁለት ሳምንት ከቆየሁ በኋላ ከክፍላችን የሚወጡ ሰዎች በዙ፡፡ ከሦስቱ የአኙዋ ልጆች አንዱ – ኝጎ ኩምቻሬ – ጓደኞቹ ላይ ሊመሰክር ተስማምቶ ወደጣውላ ክፍል ተዛወረ፡፡ ኡማን እና ኡጁሉ ክስ እስኪመሠረትባቸው ድረስ ወደሚቆዩበት ሸራተን ተዛወሩ፡፡ የሶማሊ ክልሉ ሰው ተፈታ፡፡ በምትካቸው ግን ብዙ ሰዎች መጡ፡፡

የአዳማ ዩንቨርስቲው አዱኛ ኬሶ መጣ፡፡ ገብረሚካኤል እና ሌላ ሥሙን የዘነጋሁት ሰው ከትግራይ ክልል መጡ፡፡ ሌላም ሰውዬ ከሶማሊ ክልል መጡ፡፡ አጀሌ ከቤንሻንጉል/ጉምዝ መጣ፡፡ ሁሉም የተጠረጠሩት በሽብርተኝነት ወንጀል ነው፡፡

ከሁሉም ሳቂታና ተጫዋች የነበረው አዱኛ ኬሶ ነበር፡፡ አዱኛ ከተያዘ 19 ቀናት እንደሆነው ነገረን፡፡ ‹የት ቆየህ?› አያውቀውም፡፡ ምክንያቱም፣ ወደቆየበት ቦታ ሲሄድም ሆነ ወደእኛ ሲመጣ ዓይኖቹ በጨርቅ ተሸፍነው ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ ወደሽንት ቤት ሲወሰድ እና ሲመለስ ዓይኖቹ በጨርቅ ይሸፈኑ ነበር፡፡ አዱኛ ወደኔ ክፍል ሲመጣ ግራ ዓይኑ ስር የበለዘ ነገር ነበረው፡፡ ‹ምንድን ነው?› ብዬ ስጠይቀው፣ ‹ሲይዙኝ በቡጢ የነረቱኝ ነው› አለኝ፡፡ አሁን ድረስ ያ የቡጢ አሻራ ጠባሳ ሁኖ ቀርቷል፡፡

ከጥቂት ቀናት በኋላ በፖሊስ ተደግፎ መጥቶ፣ በፖሊስ ተደግፎ 8 ቁጥር (የብቻ ጨለማ ቤት) ሲወጣና ሲገባ የቆየው መገርሳ ወደእኛ ክፍል ገባ፡፡ መገርሳ ወርቁ የሐሮማያ ዩንቨርስቲ ተማሪ ነበር፡፡ መገርሳ መጀመሪያ የተያዘው ሐረማያ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች ላይ በተወረወረ ቦምብ ተሳትፈሃል በሚል ተጠርጥሮ ነበር፡፡ መገርሳን ሐሮማያ ከተማ ተደብድቧል፡፡ ድብደባው እርቃን ነበር፡፡ እጆቹ በገመድ ተጠፍረው ጉልበቱን ያቅፍና በእጆቹ መታጠፊያ እና በቋንጃው መካከል እንጨት ያልፍና ይሰቀላል – ወፌ ይላላ፡፡ ከዚያ ይደበደባል፡፡ መገርሳ ይህንን ይነግረኝ የነበረው፣ እግሮቹ መታጠፊያ ላይ የቀረውን ሰምበር የመሰለ ነገር እያሳየኝ ነው፡፡ ‹ተንጠልጥዬ እየተሰቃየሁ ብልቴን ይጎትቱታል› ብሎኛል ሲነግረኝ፡፡ በመሐሉ ራሱን ይስታል፡፡ ‹ከዚያ ቅዝቅዝ ሲለኝ እነቃለሁ፤ ስነቃ አውርደውኝ አገኛለሁ፡፡ አሁንስ ታምናለህ አታምንም ይሉኛል፡፡ የማምነው ነገር እንደሌለ ሲያውቁ መልሰው ይሰቅሉኛል፡፡› አለ፡፡ በመጨረሻ ግን መገርሳ ተረታ፡፡
‹ሳስበው ከምሞት፣ ዕድሜ ልክ ተፈርዶብኝ በሕይወት ብኖር ይሻለኛል ብዬ አሰብኩ› አለ፡፡ ‹አዎ፣ እኔ ነኝ ቦንቡን የወረወርኩት› አላቸው፡፡ መርማሪዎቹ ተደሰቱ፡፡ ራቁቱን የሆነ ክፍል ውስጥ መሬት ላይ አጋድመውት ሄዱ፡፡ ከዚያ ‹በሕይወቴ የማይዘነጋኝ ዘግናኝ ነገር ተከሰተ› ብሎ የሚከተለውን አጫወተኝ፡፡ ቤቱ ውስጥ የዶሮ ጫጩቶች ነበሩ (የአንዱ የደህንነት ሰራተኛ መኖሪያ ቤት ውስጥ ይመስለዋል ያለው)፡፡ ጫጩቶቹ መጥተው እየተራመዱ እላዩ ላይ ይወጡበታል፡፡ መገርሳ እነርሱን “እሽ” ብሎ የሚያባርርበት አቅም አልነበረውም፡፡ እግራቸው ይበላዋል፡፡ ሲነግረኝ ‹ጫጩቶቹን ጠላኋቸው› ነበር ያለኝ፡፡ ግን ምንም ሊያደርጋቸው አልቻለም፡፡

በማግስቱ በካሜራ ፊት ሐረማያ ዩንቨርስቲ ግቢ ውስጥ የፈነዳውን ቦምብ ያፈነዳው እሱ እንደሆነ አመነ፡፡ እሱ በወቅቱ ዩንቨርስቲው ግቢ ውስጥ አልነበረም፡፡ እንዲያውም የታቀደ ረብሻ እንዳለ መረጃው ቀድሞ ደርሶት ለዩንቨርስቲ ግቢው የኦሕዴድ ጽ/ቤት ደውሎ ማስጠንቀቁን ነግሮኛል፡፡ ያ ሁሉ አልፎ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ተላልፎ ተሰጠ፡፡ ነገር ግን፣ እሱ ወደአዲስ አበባ እየመጣ እያለ ፖሊስ የእውነትም ቦንቡን ወርውሮታል ብሎ ያመነበትን ሰው ያዝኩኝ አለ፡፡ ነገር ግን ካፈርኩ አይመልሰኝ ባይ መንግሥት መገርሳን ከመክሰስ አልተመለሰም፡፡ ጽፈኸዋል በተባለው ግጥም ክስ ተመስርቶበት ‹ተከላከል› ተብሎ፣ መከላከያ ምስክሮቹን አስደምጦ ‹የነጻ› ወይም ‹ጥፋተኛ› ብይን እየተጠባበቀ ነው፡፡ አዱኛ ኬሶም በተመሳሳይ መዝገብ ‹በቄሮ አባልነት› ተከላከል ተብሎ መከላከያ ምስክሮቹን እያስደመጠ ነው፡፡

ታስሮ መፈታት ቅጣት ነው፡፡ ሰቅጣጭ በደል በሚፈፀምባት ከተማ፣ አገር ሠላም ብሎ ከሚኖር ሰው ጋር ምንም እንዳላየ፣ ምንም እንዳልሰሙ መስለው የመኖር ቅጣት፡፡

ማዕከላዊ ምርመራ ወጥቼ ስገባ፣ መታሸት ሲያስፈልገኝ ሲያሸኝ፣ ጨዋታ ሲያመምረኝ ሲያጫውተኝ የነበረው ረደላ ሸፋ እና አባሪው ሀሰን ሁለቱም ‹ነጻ ለመውጣት ወይም ጥፋተኛ ለመባል ተከላከሉ› ተብለው መከላከያ ምስክሮቻቸውን ለማስደመጥ ቀጠሮ ይዘዋል፡፡ የቤንሻንጉሉ አጄላ አራት ዓመት ተፈርዶበት ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስዷል፡፡ አቦይ ገብረሚካኤል ‹ተከላከሉ› ተብለው መከላከያ ምስክር እያስደመጡ ነው፡፡ ኡማን እና ኡጁሉም ‹ጥፋተኛ› ተብለው ፍርዳቸውን ለመመቀበል ቀጠሮ ተይዞላቸዋል፡፡

እስረኞች ይመጣሉ፣ ከሰሜን ይመጣሉ፣ ከደቡብ ይመጣሉ፣ ከምሥራቅ ይመጣሉ፣ ከምዕራብ ይመጣሉ፡፡ በሕዝብ ጥቅም ሥም ጦር መዝዞ ሥልጣን የተቆጣጠረው መንግሥት ዛሬም የፖለቲካ እስረኞች የሉኝም ይላል፡፡

በናትናኤል ፈለቀ

ሚያዝያ 17 ቀን 2006 ከምሽቱ 3፡30 አካባቢ ከቤት የሸከፍኩትን ጋቢ እና ቅያሪ ልብስ እንደያዝኩ ማዕከላዊ በተለምዶ ሳይቤሪያ በመባል የሚታወቀው የእስረኞች ማጎሪያ ሕንፃ 7 ቁጥር ገባሁ፡፡ ውስጥ 7 ሰዎች ነበሩ፡፡ እኔ 8ኛ ሆኜ ነው የተቀላቀልኳቸው፡፡ ምንም ሳልናገር ቆሜ ክፍሉን አየሁት፡፡ ሰዎቹን አየኋቸው፡፡
አንድም ቃል ሳንለዋወጥ አንደኛው “ኢትዮጵያ” ብሎ በሀዘኔታ ጭንቅላቱን ነቀነቀ፡፡
ኦቻን ኦፕዮ የአኝዋክ ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ በ1996 በጋምቤላ የተቀሰቀሰውን ግጭት ሸሽተው ወደአሁኗ ደቡብ ሱዳን ከተሰደዱት ኢትዮጵያውያን መካከል ነበር፡፡ በወቅቱ የተከሰተውን ችግር ተከትሎ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ይፈፅም የነበረውን ግድያ በመሸሽ ለቀናት ጫካ ውስጥ ተደብቆ ከቆየ በኋላ ነበር ቀናትን የፈጀ የእግር ጉዞ አድርጎ ደቡብ ሱዳን የገባው፡፡ ከጁባ አቅራቢያ የአለ የስደተኞች ጣቢያ ውስጥ ከ8 ዓመት በላይ የቆየው ኦቻን ቤተሰብ መሥርቶ፣ ሁለት ልጆችን ወልዶ በጁባ የተረጋጋ ሕይወት መኖር ጀምሮ ነበር፡፡
የ1996ቱ የጋምቤላ ቀውስ በተቀሰቀሰበት ወቅት ክልሉን በርዕሰ ብሔርነት ይመሩ የነበሩት አቶ ኦኬሎ ኦኳይ በደቡብ ሱዳን መንግሥት ተይዘው ለኢትዮጵያ መንግሥት ተላልፈው ሲሰጡ ከጁባ አብረዋቸው የታሰሩት የአኝዋክ ተወላጆች መካከል ኦቻን ኦፕዮ ነበር፡፡
ወደደቡብ ሱዳን ሲሸሽ ጫካ ውስጥ እሾሃማ የዛፍ ቅርንጫፍ የቀኝ ዓይኑን መቶት የማየት ችሎታውን ቢጋርድበትም የቀረችውን የማየት ችሎታውን በአኝዋክኛ የተተረጎመውን መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበ የእስር ግዜውን ያሳልፋል፡፡ (በነገራችን ላይ መጽሐፍ ቅዱስን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደአኝዋ የተረጎሙት ኡመድ አግዋ በአሁኑ ወቅት በሽብር ወንጀል ተከሰው ቂሊንጦ ይገኛሉ፡፡)
ኦቻን ሲበዛ ሠላማዊ ሰው ነው፡፡ የሁለት ልጆቹ ነገር አብዝቶ ያሳሰበው ቀን ግን ከሰው ጋር መነጋገር አይፈልግም፡፡ አንድ ቀን ድንገት ብቻውን ስቅስቅ ብሎ ያለቅስ ጀመር፡፡ ሰባት ቁጥር በግዜው የቀረነው እሱ፣ እኔና ዘግየት ብሎ የተቀላቀለን ቢልሱማ የሚባል የሐሮማያ ዩንቨርስቲ ተማሪ ነበርን፡፡ ሁለታችን በጣም ተደናግጠን ምን እንደሆነ ጠይቀነው ሊነግረን ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ቆይቶ ሲረጋጋ ልጆቹ እንደናፈቁት እና ምን አጥፍቶ እንዲህ ያለ ፈተና እንደገጠመው እንዳልገባው እያማረረ አጫወተኝ፡፡
በነኦኬሎ ኦኳይ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ ሆኖ ቀድሞ ቂሊንጦ የወረደው ኦቻን ነበር፡፡ ከጥቂት ግዜያት በኋላ እኔም በነሶልያና ሽመልስ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ ሆኜ ቂሊንጦ ስወርድ ኦቻንን ዞን3 አገኘሁት፡፡ እንደመጀመሪያው ሁሉ ተንከባክቦ ግቢውን አላመደኝ፡፡
ኦቻን የአኝዋ አስተማሪዬም ነበር፡፡ ለቤት የመጀመሪያ ልጅ መሆኔን ስለሚያውቅ በአኝዋ ባሕል እንደሚደረገው ኡመድ እያለ ነው የሚጠራኝ፡፡ ትንሽ የማይባሉ የአኝዋ ቃላትንም አስተምሮኛል፡፡
የአኙዋኩ ጓደኛዬ የተከፈተበት የሽብር ክስ የአገር ግዛት አንድነትን ለማፍረስ ሞክሯል በሚል ተቀይሮለት ጥፋተኛ ተብሎ ቂሊንጦ ፍርዱን በመጠባበቅ ላይ ይገኛል፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ እስር ስገባ ያስተዋልኩት በሐዘን ተሞልቶ “ኢትዮጵያ!” ሲል ያማረረው ፊቱ እስከ ሕይወቴ ፍፃሜ አብሮኝ ይዘልቃል፡፡ ይህችን አጭር ጦማር ያለህበት ድረስ መንፈስ ይዞት ይመጣ እንደሆን ይነ ፑዋ! ኦሎ ቦንጎ! ብዬሃለሁ፣ ኦቻን ኦፒዮ፡፡

በፍቃዱ ኃይሉ

የሥም ነገር ሳልወድ በግዴ ያፈላስመኛል። ሥም ተራ መለያ መጠሪያ ብቻ ነው ብዬ አልቀበልም። ምናልባት መጀመሪያ ላይ እንዲያ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን አሁን፣ ሥም በባሕልና የሥልጣኔ ዝግመተ ለውጥ ሒደት (evolution of civilizations) ውስጥ ብዙ ውስብስብ ነገሮችን እያነገበ በጊዜ ባቡር ተሳፍሮ ውስብስብ ደረጃ ላይ ደርሷል። ሥም የባሕል መገለጫ፣ የፖለቲካ አመለካከት መንፀባረቂያ፣ የወላጆች ለልጆች ውርስ ነው። ለዚያም ይመስለኛል “ሥምና ማንነት” የሚለው ጉዳይ የመጽሐፍ ምዕራፍ እና የጥናት ርዕስ ለመሆን እየበቃ ያለው።  አባቶቻችን በፈረንጆች ‘የሊትሬቸር’ አጻጻፍ ደምብ ስላልጻፉልን ፍልስፍና መስለው ያልታዩን አፈላሳፊ አባባሎች አሏቸው። የሊቃውንቱ “ሥሙ ይመርሖ ኀበ ግብሩ” (ሥሙ ተግባሩን ይመራዋል) የምትለው አባባላቸው አሁን ምዕራባውያን እያጠኑት ያሉት ጉዳይ ላይ እነርሱ የደረሱበት ድምዳሜ ነው። በነገራችን ላይ በተቀራራቢ ሮማውያንም ‹nomen est omen› (ሥም ዕጣፈንታ ነው) የሚሉት አባባል አላቸው፡፡ ሳይንቲስቶች «ሰው ወደሥሙ ወይም ከሥሙ ወዲያ (እየተጎተተ ወይም እየተገፋ) የሚኖር ብኩን ፍጡር ነው» ወደማለቱ እየዳዳቸው ነው። ለመሆኑ አንድ ሰው ለመለያ ይሆነው ዘንድ የተሰጠው ሥም ማንነቱን ያሳብቃል? ባሕሪው ላይ ወይም ተግባሩስ ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል?

የሥም ቅርፅ

ሥም ከአገር አገር ብቻ ሳይሆን ከዘመን ዘመን ቅርፁና ፀባዩን እየቀያየረ ይሄዳል። ለምሳሌ ምዕራባውያን ‘የቤተሰብ ሥም’ የሚሉት እኛ የለንም፤ አንዳንዶች የጎሳ ሥም እሱን ይተካል ይላሉ። በጊዜ መሥመር ደግሞ ለምሳሌ በኢትዮጵያ በ19ኛው ክ/ዘመን (ከ1900ቹ በፊት) የኢትዮጵያውያን ሥም የሚጻፈው (የሚገለጸው) ‘ከአያት ሥም➡ የአባት ሥም ➡ የልጅ ሥም’ በሚለው ቅደም ተከተል ነበር። ከዚያ ወዲህ ግን (‘የእከሌ ልጅ’ ዘመን አልፎ፣ ‘የእከሌ አባት’ ዘመን ሲጠባ) በተቃራኒው ተደርጓል። በቱርክ እ.ኤ.አ. ከ1943 በፊት የቤተሰብ ሥም የሚባል ነገር አልነበረም። አንዱን ሰው ከሌላኛው ለመለየት ሲባል እስከ ሦስት ሥሞች ድረስ ይወጡለትና በዚያ መደዳ (በእኛ እስከ አያት ሥም በምንለው መንገድ) ይጠራ ነበር። በዚህ የአሰያየም ስርዓት የአባትና የልጅ ሥም ምንም የሚያዛምዳቸው ነገር የለም። ለምሳሌ የቱርክ አባት የሚባለው አታቱርክ (Atatürk) ሥሙ ሙስጠፋ ከማል ነበር። አታቱርክ የተጨመረው ኋላ ለክብሩ ሲባል ነው። የአባቱ ሥም ደግሞ አሊ ሪዛ ነበር። በቱርክ የተጠፋፉ ዘመዳሞች በሥም ተፈላልገው የመገናኘት አማራጭ አልነበራቸውም ማለት ነው። በሌላው ባሕል የልጅ ሥም፣ የአባት ሥም፣ የቤተሰብ ሥም… የምንለው ነገር ዝምድና መቁጠሪያም ጭምር ነው ማለት ነው፡፡

በአገራችን በተለያዩ ማኅበረሰቦች የተለያየ ዓይነት የሥም አወጣጥ አላቸው። ለምሳሌ በጋምቤላ የአኙዋክ ብሔረሰብ ሥም አወጣጥ ሥሙን ሰምቶ ስለሰውዬው ጥቂት ቤተሰባዊ መረጃ ማግኘት ይቻላል። በአኙዋክ፣ የመጀመሪያ ልጅ ኡመድ ይባላል፤ ሁለተኛ ኡጁሉ፣ ሦስተኛ ደግሞ ኦባንግ እያለ ይቀጥላል። አንዳንዴ አባትና ልጅ አንድ ዓይነት ሥም ሊኖራቸው ይችላል። ታላላቆቹ ሴቶች ሆነው መጀመሪያ የሚወለድ ወንድ ኦማን ይባላል። ለምሳሌ እኔ ከአኙዋክ ቢሆን የተወለድኩት ኦማን እባል ነበር እንደማለት ነው።…

በአማራ ተወላጆች ዘንድ ደግሞ ትንሽ ለየት ይላል። ለምሳሌ መንዞች “ርስትና ውትድርና ይወዳሉ” ይባልላቸዋል። ይህም በሥማቸው ሳይቀር ይስተዋላል። ለምሳሌ “ሸዋጉልቱ” የመንዜ ሥም ነው። አምበርብር፣ ደምሰው፣ ዳምጠው፣ አሸብር፣ የመሳሰሉትም የመንዜ ሥሞች ናቸው። ጎንደሬ ደሞ “ሹመት ይወዳል” ይባላል። የጎንደሬ ሥሞች ሹመቴ፣ መኳንንት ወይም መኮንን የመሳሰሉት ናቸው (ወይም ነበሩ)። ቀደም ብዬ እንዳልኩት የሥም አወጣጥ እንደጊዜው ይለዋወጣል። ጎጃም የሄድን እንደሆነ ደግሞ ከልጅ እስከ አባት (ወይም አያት) ያለው ሥም ተገጣጥሞ ዓረፍተ ነገር የሚሰጥበት ጊዜ አለ። በጣም ታዋቂ ከሆኑት መካከል ብንጠቅስ እንኳ ሐዲስ ዓለምአየሁ፣ በዕውቀቱ ሥዩም፣ ፍቅር ይልቃል፣ እያደር አዲስን ማግኘት ይቻላል።

ሥም እና ፖለቲካ

ሥም የፖለቲካ መሣሪያም ነው። የአብዮቱ ሰሞን የተወለዱ ልጆች ‘አብዮት’፣ ‘ትቅደም’… የሚል ሥም ተሰጥቷቸው ዕድሜያቸውን እንኳ እንዳይደብቁ ሆነዋል። አሁንም ያ ባሕል ቀጥሎ “ሕዳሴ” ከሥም ዝርዝሮች ውስጥ ገብቷል። የኦሮሞ ብሔርተኞች ‘የአማራ’ ሥማቸውን እየቀየሩ ቢሊሱማ (ነፃነት)፣ ኒሞና (አሸናፊ) የመሳሰሉት የወጣት ‘አክቲቪስቶች’ ተመራጭ ሥሞች እየሆኑ ነው። ኦቦ ሌንጮ (“አንበሳው” እንደማለት) ለታ (ከዮሐንስ ለታ) እና ብዙዎቹ የኦነግ አንጋፋዎችም ሥሞቻቸውን በመቀየር ነው ትግላቸውን የጀመሩት። በዕውቀቱ ሥዩም የአያቱ ቀዳማይ ሥም በዻዻ መሆኑን መጥቀሱ የኦሮሞ ብሔርተኝነትን ለመተቸት እንደነፃ ፈቃድ ሆኖለታል (ወይም ተጠቅሞበታል)። ዮናታን ተስፋዬ ደግሞ የአባቱን ቀዳማይ ሥም (ቴሬሳ) ፈልጎ የተጠቀመው የኦሮሞ ብሔርተኝነትን በአዎንታዊ መንገድ መረዳቱን ለማመልከት ነበር። በተመሳሳይ በ‘ያ ትውልድ’ ዘመን ሥምን ለፖለቲካ ዓላማ ራስን ለመደበቅ ሲባል መቀየር የተለመደ ነበር። ሕወሓቶች የሞቱ ጓዶቻቸውን ሥም ይወርሱ ነበር። ለገሰ ዜናዊ መለስ ዜናዊ እንደሆኑት ማለት ነው። በሕወሓት ለፖለቲካ ዓላማ ስዩም መስፍን ከአረቦች (ሶርያዎች) እርዳታ ለማግኘት ራሳቸውን ሙስሊም አስመስለው ለማቅረብ የአባታቸውን ሥም ሙሳ ነው ብለዋል። ብዙዎቹ የኦህዴድ ሰዎችም ከምርኮ ወደትግል ሲገቡ የ“አቢሲኒያ” ሥሞቻቸውን ወደ “ኦሮሞ” ቀይረዋል።

ሥምን ለፖለቲካ አገልግሎት መቀየር በዓለም ዙሪያ የተለመደ ነው። አምባገነኑ ሞቡቱ ሴሴ ሴኮ ‘የአውሮጳውያን’ ነው ያሉትን ሥማቸውን ቀይረው ነው ሴሴ ሴኮን በማስጨመር የትግል ሥም ያገኙት። በአገራቸው ዛየር (የአሁኗ ኮንጎ) የክርስቲያን ሥም (Middle Name የሚባለው) ‘የእብራይስጥን ሥም’ ለአፍሪካውያን ሲሰጥ የተገኘ ቄስ እስከ 5 ዓመት የሚደርስ እስር እንዲቀጣ የሚያደርግ ሕግ አውጥቷል። ጥቁር አሜሪካዊው ታጋይ ማልኮም ኤክስ የቤተሰቡን ሥም በ‘X’ የተካው እና ሌሎችም አጋሮቹ እንደዚያው ያደረጉት “የነጮች” ነው ያሉትን የክርስትና ሥም ለመቃወም ነበር።

ሥም እና ሃይማኖት

መጤ ሃይማኖት ነባር ባሕሎችን ሁሉ ደምስሶ የመተካት አቅሙ ኃያል ነው። ክርስትና እና እስልምና የዓለም ሥም አወጣጥ ቅርፅን የለወጡት በዚሁ ኃይላቸው ነው። በዓለማችን ላይ በብዛት ወንዶች የሚጠሩበት ሥም ‘መሐመድ’ ነው የሚል ነገር ማንበቤ ትዝ ይለኛል። በአገራችን ወላጆች ለልጆቻቸው ሥም ሲያወጡ ወይ አምላካቸውን መጥቀስ ወይም ከቅዱስ ባለታሪኮቻቸው የአንዱን ታሪክ መጥቀስ ይቀናቸዋል። በሱፍቃድ (በእግዜር ፍቃድ)፣ ዋቅጅራ (እግዜር አለ)፣ ገብረእግዚኣብሔር (የእግዜር ሥራ)… ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው።

በቅዱሳን ባለታሪኮች ልጅን መሰየም በተለይ አሁን አሁን ፋሽን እየሆነ መጥቷል። አገር በቀል ሥሞችን ለልጆች ማውጣት ልጆቹን “ፋራ” (ወይም “አራዳ” ያልሆኑ) የሚያሰኝ ይመስላል።

በሌላ በኩል በቀድሞ ጊዜ ለንግሥና ሲባል ሥምን መቀየር የተለመደ ነበር። ብዙ ጊዜ ንግሥናን በጳጳሳት ተቀብቶ ለማፅደቅ ሲባል በክርስትና ሥም መጠራት ደንብ ነበር። (ነገሥታት ራሳቸውን ሥዩመ-እግዚአብሔር ይሉ ነበር። ስለዚህ ንግሥና ፖለቲካዊ ብቻም ሳይሆን ሃይማኖታዊም ነበር) ተፈሪ መኮንን [ቀዳማዊ] ኃይለሥላሴ የተባሉት በዚያ መንገድ ነው። “ቴዎድሮስ የተባለ ንጉሥ እስከ እስራኤል ይገዛል” የተባለውን ትንቢት ወይም ጥንቆላ ተከትሎ ነው ካሣ ኃይሉ ራሳቸውን [ዳግማዊ] ቴዎድሮስ ብለው ያነገሡት። ቀዳማዊ ቴዎድሮስም ሥማቸውን ያገኙት በትንቢቱ መሠረት እሰከ እስራኤል የመግዛት (ካልሆነም ትንቢቱን ሰምተው በሥም የሚግገዙላቸው እንዲያገኙ) ተመኝተው ነው። አውሮጳውያን አፍሪቃዊ ኃያል የክርስቲያን መንግሥት መሥርቷል ብለው በአንዲት ደብዳቤ መነሻ ብዙ ያወሩለት የነበረውን ቄስ ዮሐንስ (Prester John) ለመሆንም ሲባል ነው እስከ አራተኛ የተደረሰው። ዐፄ ዮሓንስ እና የወሎ ሙስሊሞች የገቡበት ቁርሾ መነሻም የዐፄው እንደሥማቸው የማደር ምኞት ይመስለኛል።

ሥም እና ስርዓተ—ፆታ

ሥም ስርዓተ-ፆታን የሚገልፅበት ሁኔታም ቀላል አይደለም። ወንዶች በአማራው ተወላጅ ዘንድ በጥቅሉ ምናባዊ ጀግንነትን የሚያጎናፅፍ ሥም ይሰጣቸዋል። ለምሳሌ ወንዳፍራሽ፣ ናደው፣ ሺመክት፣ መኩሪያ፣ የመሳሰሉትን ሥሞች መጥቀስ ይቻላል። በኦሮምኛ ሌንጮ (አንበሳው)፣ ኬራንሶ (ነብሩ፣ ደፋሩ)፣ ዋንጎ (ቀበሮው) የሚሉ በኃይለኛ አራዊቶች ሥም ለወንዶች የሚሰጡ ስያሜዎች ጀግንነትን ለወንድ የማልበሱ ማኅበራዊ ትውፊት አካል ናቸው። ጫላ (ቀዳሚው)፣ ሁንዳራ/ኢራና (የበላይ)፣ ኩማራ (ሺመክት) የመሳሰሉትም የተጠቀሰውን ምናባዊ ጀግንነት አልባሽ ኦሮምኛ ስያሜዎች ናቸው። በሲዳምኛ አዳቶ (ደፋሩ)፣ ዳፉርሳ (የማይዳፈሩት) የመሳሰሉት ሥያሜዎች የላይኞቹ ዓይነት ሚና አላቸው። በሌሎቹም ቋንቋ እና ባሕሎች ውስጥ ተመሳሳይ አጠራሮች አሉ።

ለሴቶች ሲሆን ውበታቸውን፣ ወይም በቁስ የሚተመን ዋጋቸውን የሚገልፅ ሥም ይሰጣቸዋል፦ መድፈሪያሽ ወርቅ፣ ሺብሬ፣ ወርቂቱ፣ ብሪቱ፣ ሸጊቱ፣ ቆንጂት…የሴቶች ሥም አወጣጥ ሴቶችን በአትክልትና ፍራፍሬ የሚመስልበትም ጊዜ ቀላል አይደለም፤ አበባ፣ ወይኒቱ፣ ትርንጎ፣ ብርቱኳን፣ ሸዊት (በትግርኛ “እሸት” ማለት ነው) ጥቂት ምሳሌዎች ናቸው። በኦሮምኛ ቢፍቱ (ብሩህ፣ ፀሐይቱ/ጣይቱ)፣ ፋኖሴ (መብራቴ)፣ መጋሌ (ጠይም/ቆንጆ)፣ ዱንጉጄ (ሽንኩርት፣ አጭር ቆንጆ)፣ በከልቻ (ኮኮብ፣ ለዓይነ ቆንጆ) የመሳሰሉት ሥሞችና በሲዳምኛ ዳንቺሌ (ቆንጆ፣ ፀባየ ሸጋ)፣ ደራርቱ (አበባ፣ ፍካት (ኦሮምኛም ነው)) ሴትን በውበቷ የመግለፅ ትውፊታዊ ወግ ያሳያሉ።

ሥም እና የቤተሰብ ታሪክ

ሥም አንዳንዴ የሐዘን መግለጫ ነው። አባቱ (ተፀንሶ እያለ ወይም በልጅነቱ) ወይም ታላቅ ወንድሙ የሞተበት ልጅ ለምሳሌ በአማርኛ ምትኩ፣ ማስረሻ… ይባላል፤ በትግርኛ ካልኣዩ፤… ታላላቆቹ ሲወለዱ እየሞቱ እሱ ግን ያንን መሰናክል ያለፈ ልጅ ለምሳሌ በአኙዋክ ኞም ይባላል፤ በሲዳማ ሪቂዋ ይባላል።

ሥም አወጣጥ ልጁ በተወለደ ጊዜ ወላጆች የነበራቸውን ግንኙነት፣ የኢኮኖሚ ሁኔታ እና ወዘተ የሚናገርበትም ሁኔታ አለ፤ ለምሳሌ አስማማው፣ አስታርቄ… የመሳሰሉት ሥሞች ብዙ ጊዜ የሚወጡት እየተጥጣሉ (በተለይ በልጅ እጦት) የነበሩ ጥንዶች የልጅ መገኘቱን ተከትሎ ሲስማሙ ነው። ወላጆች ልጅ ሲወልዱና የጥሩ ዕድል (በተለይ የሀብት) መምጣት ከተገጣጠመ ልጃቸውን ሀብታሙ፣ ጥጋቡ፣… ብለው ሊሰይሙት ይችላሉ። በተቃራኒው ከገጠማቸው ደግሞ ያንኑ የሚያንፀባርቅ ሥም ይሰጡታል፤ ለምሳሌ ‘በድሉ’ የሚለው ሥም በዕድሉ ይደግ ከሚለው የመጣ ነው፤ ወይም ሳይታቀድ ከመጣ ነው። በኦሮሞ ትውፊት ተጨማሪ ልጅ የማይፈልጉ መሆኑን ለመግለጽ ወላጆች ለ“መጨረሻ” ልጃቸው ጉታ የሚል ሥም ያወጣሉ።

«ሥምህን ንገረኝና ማንነትን እነግርሃለሁ»

የኒው ሳይንቲስት ጋዜጠኛ ጆን ሆይላንድ “nominative determinism” (ሥም አመጣሽ ቁርጠኝነት) የሚለው ነገር አለው። ‘ሥም አመጣሽ ቁርጠኝነት’ የሚወክለው በሥማቸው ተገፍተው ለስያሜያቸው የሚስማማ ሙያ ሲከተሉ ነው። ለምሳሌ በዕውቀቱ ሥዩም ኃይለኛ ቦክሰኛ ቢሆን ኖሮ ሥሙ ከሙያው ጋር አይሰምርም እንል ነበር። በቡጢው ሥዩም ይሆን ነበርና። ስለዚህ የበዕውቀቱ ‘ሥም አመጣሽ ቁርጠኝነት’ ኋላ ቀር የሚለውን ስርዓት (social order) በነውጥ/ነፍጥ ሳይሆን በዕውቀት በመሞገት መንገሥ/መሰየም ነው።

ብዙ መንግሥቱ፣ ንጉሡ የተባሉ ሰዎች መራኄ መንግሥትነት ማዕረግ ሳያገኙ አንድ መንግሥቱ ኃይለማርያም ቦታውን መቆናጠጡ ብቻ መንግሥቱ የተባለ ሰው ሁሉ የመንግሥት ኃላፊ ይሆናል ማለት ባይቻልም ሥማቸው ግብራቸውን ቀድሞ እንዲመራው በማድረጉ ረገድ ተፅዕኖ መፍጠር ይችላል በሚለው ግን መስማማት እንችላለን፡፡

በአማራው ማኅበረሰብ ዘንድ ‹ደመላሽ› የሚለው ሥም የሚሰጠው “ደም የተቃቡ” ቤተሰቦች መካከል ከአንደኛው ወገን ተበቃይ ባልነበረበት ጊዜ ለተወለደ ልጅ ነው፡፡ የዚህ ልጅ ዕጣፈንታ ባስተዳደግ ይወሰናል፡፡ ሥሙን ያወጡለት ሰዎች ሥሙን ለምን እንዳወጡለት ብቻ ሳይሆን ምን እንዲያደርግላቸው እንደሚፈልጉም ጭምር እያስተማሩት ነው፡፡ ስለሆነም፣ አድጎ “ጠላት” የሚለውን ወገን ለመግደል መሠማራቱ ሰፊ ዕድል ያለው የሕይወቱ ምዕራፍ ነው የሚሆነው፡፡

ሥም እና ማንነት ግንኙነት አላቸው የሚሉ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት፣ “ሥማችን – ወይም ሰዎች ሥማችንን ሲሰሙ በሚያሳዩት ግብረ-መልስ ወይም የማንነት ግምት ላይ ተመሥርቶ ባሕሪያችንን ይወስናል፡፡” ወደድንም ጠላንም በሥማችን ብቻ ሰዎች ዘውጋዊ ማንነታችንን፣ የቤተሰባችንን ሁኔታ፣ እና ሌሎችም መሠረታዊ ግምቶችን ስለኛ ያሳልፋሉ፡፡ እኛም ይህንኑ ስለምንረዳ የሰዎቹን ግምት ለማጠናከር ወይም ለማስተባበል የበኩላችንን ጥረት በማወቅም፣ ባለማወቅም ማድረጋችን አይቀርም፡፡

ሥም በባለቤቱ ላይ የሚያመጣውን ማንኛወንም ዓይነት ተፅዕኖ ለመቀነስ የተለመደ-ሥም (popular name) መስጠት እንደመፍትሔ ይጠቆማል፡፡ ልጆች በሥማቸው ማንነታቸው እየተገመተ፣ እነሱም በምላሹ በሥማቸው እና ሥማቸውን ሰምተው ሰዎች በሚያሳልፉት ግምት ተፅዕኖ ሥር እየወደቁ ‹የሥማቸው ፍሬ› እንዳይሆኑ ሲባል ለልጆች በሚያድጉበት አካባቢ የተለመደ የሚባለው ዓይነት ሥም ቢሰጣቸው የገዛ ሥማቸው ሰለባ ከመሆን ይድናሉ፡፡ 


እንደ ዋቢ:-
– የነጋድራስ ገ/ሕይወት ባይከዳኝ ድርሰቶች፣
– Atatürk (biography), by Andrew Mango
– Wax and Gold, by Donald Levine
– ፍቅር እስከ መቃብርን የጻፉት «ሐዲስ» ናቸው ወይስ «ዓለማየሁ»? (የሚከራዩ አማት እና ሌሎች)፣ በዳንኤል ክብረት
– ሉኣላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ፣ በገብሩ አሥራት
– ሥምና ማንነት (ከአሜን ባሻገር)፣ በበዕውቀቱ ሥዩም
– Typology of Oromo Personal Names, by Tesfaye Gudeta Gerba
– እና የተለያዩ ድረገጾች እና ሌሎችም…

በአፍሪካ አሜሪካውያን የሲቪል መብቶች ትግል ውስጥ እና በደቡብ አፍሪካ ነባር ጥቁሮች ከመጤ አፍሪካነሮች የተነጠቁትን የዕኩል ሰውነት መብት ለማስመለስ ሲታገሉ፣ ጥቂት የማይባሉ ነጮች (ወይም አፍሪካነሮች) የትግላቸው አጋር ሁነውላቸው ነበር። ሌሎች ጥቂቶች በደሎቹን ምክንያታዊና ተገቢ ለማድረግ (to justify) ተከራክረዋል። ብዙኃኑ ግን በገለልተኝነት እና በስጋት ተመልክተውታል። ከጥቁሮቹ ታጋዮች መካከልም ከፊሎቹ ለዕኩል የሰውነት ማዕረግ ታግለዋል። ከፊሎቹ ነጮቹን ለመበቀል ታግለዋል። ዞሮ፣ ዞሮ ግን ሁሉም ነባሩን ትርክት እና ተቀባይነት የነበረውን (mainstream) አስተሳሰብ ማፈራረስ ነበራቸው። በዚህ ግዜ ነጮቹ ቀድሞ የነበራቸውን የተለየ መብት ከጥቁሮች ጋር መጋራታቸው መብታቸውን እንደመነጠቅ ቆጥረውታል። ለምሳሌ ቅድሚያ ይሰጣቸው የነበረውን አገልግሎት ከጥቁሮች ዕኩል እንዳደራረሳቸው እየተሰለፉ እንዲያገኙ መገደዳቸውን እንደመብት ነጠቃ ይቆጥሩታል።

እነዚህ ተግዳሮቶች መገፋፋት ይፈጥሩ ነበር። በዚህ ሳቢያ ከነጮቹም፣ ከጥቁሮቹም ወገን አብረን መኖር አንችልም የሚል ሰውነትን የመጠራጠር ዝንባሌ ታይቷል። በአሜሪካ እነማልኮም ኤክስ ይመሩት የነበሩት እንቅስቃሴ የነጭ የሆነውን ሁሉ መጠየፍን እንደስትራቴጂ የቆጠረ ነው። የነሱ ተቃራኒ ዕኩያ የሚባለው ኬኬኬ የሚባሉት የነጮች ጥቁር ተጠያፊ ቡድን ነው። የማልኮሜክስ ‘ኔሽን ኦቭ ኢስላም’ እና ‘ኩ ክላክስ ክላን’ አንዴ ስምምነት ላይ ደርሰው ነበር። ጥቁሮቹም ነጭ የማያዩበት የጥቁር ዓለም፣ ነጮቹም ጥቁር የማያዩበት የነጭ ዓለም ሊመሠርቱ። አንዱ ሌላኛውን ለማግለል እንደመስማማት።

በቀድሞዋ አሜሪካ ሰሜኖቹ “ነጻ አገሮች” ሲሆኑ ደቡቦቹ “ባሪያ አሳዳሪ” ነበሩ። ሶሻሊስቶቹ በወቅቱ በሰሜን የነበረውን የጭሰኝነት ሁኔታ እያዩ በሰሜን ያለው የጭቁን ሠራተኞች ሁኔታ እና በደቡብ ያለው የባሪያዎች ሁኔታ አንድ ነው እስከማለት የሚደፍሩ ነበሩ – በመደብ ጭቆና ትንተና። ነገር ግን በወቅቱ ከደቡብ ባርነት ኮብልለው ወደሰሜን ጭሰኝነት የሚፈልሱ እልፍ ሰዎች ቢኖሩም፣ ከሰሜን ጭሰኝነት ወደደቡብ ባርነት የኮበለሉ ሰዎች አልነበሩም።

ሌላኛው ፈታኝ ነገር ያንን ጥቁሮችን የሚያንኳስስ ስርዓት የሚደግፉ ጥቁሮች መኖራቸው ለነጭ አስተባባዮች ምቹ ሁኔታ መፍጠሩ ነበር። ማልኮም ኤክስ በባርነት የነበሩ ጥቁሮችን በሁለት ይከፍላቸው ነበር። የቤት እና የመስክ ኔግሮዎች (house and field negroes) ብሎ። የቤት ኔግሮዎቹ ጥቁር ቢሆኑም ከጌታው የሚተርፈውን ከስር ከስር የመቋደስ ዕድሉ ነበራቸው (they were privileged)። ተመችቷቸዋል። ስለዚህ፣ አብዛኛውን ፍዳ እንደሚቀምሱት የመስክ ኔግሮዎች ስርዓቱን አይቃወሙትም፣ እንዲያውም በደሉን በሰበብ ያለባብሱለታል።

እንዲህ ዓይነቱ የታሪክ ትርክት መገፋፋት ኋላ ላይ የዕኩል ሰውነት ማዕረግ ለማግኘት ይታገሉ ለነበሩት ለነማርቲን ሉተር ኪንግ ፈታኝ ነበር። በግለታሪኩ ላይ ኪንግ የሲቪል መብቶች ትግሉ አንዱ ፈተና ይህ እንደነበር ገልጿል። መጨረሻ ላይ ስኬታማ የሆነው ግን፣ የአግላዮቹ ሳይሆን የአካታቾቹ ትግል ነው። ጥቁሮቹ ዕኩል መብቱን ሲያገኙ ቀድሞ ነጮቹ ይፈሩት እንደነበረው ዓይነት ጥፋት አልደረሰም።

በደቡብ አፍሪካ ኤኤንሲ ጥቁሮች ብቻ ሳይሆን ነጮችንም በአባልነት ይቀበል ነበር። የነማርቲን ሉተር ኪንግ እንቅስቃሴም በርካታ ነጭ አጋሮች ነበሩት። ማልኮም ኤክስ ከመገደሉ ጥቂት ቀደም ብሎ ስለሚፀፅተው ነገር ሲናገር አንዲት ታዳጊ ልጅ ጠቅሷል። ከዓመታት በፊት ማልኮም የአግላዩ ትግል ሊቀ ጳጳስ እይያለ አንዲት የ10 ዓመት ሕፃን ልጅ እቅፍ አበባ ይዛ ለጥቁሮች ትግል አጋርነቷን ለማሳየት ስትወጣ ‘ሂጅ ከዚህ፤ እኛ ከነጮች ጋር አጋርነት የለንም’ ብሎ አባሯት ነበር። ኋላ፣ እየበሰለ ሲመጣ ተፀፅቷል።

እኛ አገር በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የፆታን ጨምሮ፣ ከፊሉ በመደብ፣ ከፊሉ በማንነት፣ ከፊሉ በመደብ እና በማንነት ምክንያት በሚሉት መሠረት (መሠረቱን ባለሙያዎች በጥናት ሊበይኑልን ሲገባ እኛ ባላዋቂነት ጭቃ እየተለቃለቅንበት እንገኛለን፣ ለማንኛውም) ለዘመናት በገዢዎች እና በተገዢዎች መካከል (ወይም ዘመንና በሕል ባፈረጠማቸው እና ባንኳሰሳቸው የማኅበረሰብ ክፍሎች /ምሳሌ ወንዶች እና ሴቶች/) ለደረሱት በደሎች እና በዘለቄታው ላስከተሉት በማንነት ላይ የተመሠረተ የተጠቃሚነት ጉዳትን ለማስተካከል (undoing sustained system of repression) አንዱ የሌላው አጋር በመሆን አካታች የመብት ትግል በማድረግ ፈንታ አግላይ ትግል እያደረግን ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ አማራጭ እያለን፣ ሁሉንም ተሸናፊ የሚያደርገውን አማራጭ እየተከተልን እንገኛን።

ብዙ ጊዜ አጋርነትን አለመከተል ጦስ አለው። “ችግር የለም” በሚል በክህደት (denial) የተጀመረው፣ ወደፍረጃ ወይም መጥሌ (prejudice) ያድግና ውጤቱ የእርስበርስ እልቂት ይሆናል። ለዕኩል ዕድል እና መብት የሚታገሉት ቡድኖች በአግላይ ትርክት ጠላት የሚል ሥም የሚያወጡለት ቡድን ስለሚኖረው “ተቃራኒያችን” የሚሉትን ወገን ይገፋሉ። በሌላ በኩል ያንኛው ወገንም አንዳንድ ነባር ጥቅሞቼ ሊሸረሸሩብኝ ነው፣ ከሌሎች የዕኩል ባለመብቶች ጋር ልጋራው ነው በማለት የአፀፋ ግፊት ይገፋሉ።

የአንዱ እምነት ተከታይ ይሄ በደል ነበረብኝ፣ አለብኝ፣ በዘዴ እንዲቀጥል እየተደረገብኝ ነው ሲል፤ አንዱ ብሔርተኛ በማንነቴ ምክንያት እንዲህ ዓይነት በደል ይደርስብኝ ነበር፣ አሁንም አለብኝ፣ በዚህ አካሔድ ወደፊትም በደሉ ይቀጥልብኛል ሲል፤ አንዷ ሴት በመሆኔ ብቻ ወንዶች በቀላሉ የሚያገኙትን መብትና ዕድል ተነፈግኩ ስትል፣ «እኔ አለሁልህ/ሽ» በማለት ሰው ሠራሽ የእምነት እና የማንነት ድንበሮችን መስበር ካልቻልን ለሰውነት ማዕረግ ብቁ ነን ማለት አይቻልም። ተበዳይም በአርቲፊሻል ሰበቦች ላይ ተመሥርቶ ‘አንተማ በድለኸኛል፣ ወግድልኝ’ ካለ ትግሉ የሚገባውን የሰውነት ማዕረግ ለማግኘት ሳይሆን በተራው የሌሎችን ለመግፈፍ ነው ማለት ነው። ዳር ላይ ቁሞ ችግሩን ለመፍታት የሚፍጨረጨሩትን ፀጉር እየሰነጠቁ በማብጠልጠልም ግድግዳው አይፈርስም። የሚከፋፍለን ግድግዳ ፈርሶ፥ የሚያቀራርበን ድልድይ የሚሠራው እያንዳንዳችን ሌሎች በሚያደርጉት ትግል ውስጥ አጋርነታችንን በተግባር መግለጽ ስንችል ነው።

መጤ ሃይማኖት፣ ከመጤ ሃይማኖት በመምረጥ፣ (ግን በመሠረቱ ለገዢዎቹ ዋናው ሃይማኖቱ ሳይሆን በሥመ ሥዩመ–ፈጣሪነት የገዢነት ዕድል እና ተገዢ የማግኘት ጥረት ነው።) በወንዜ ማንነት ላይ በመመሥረት አገር ሲገዙ የነበሩ ሰዎች በነበሩበት አገር ውስጥ ያንን የሚያስተባብሉ (justify-ers) መኖራቸው አይገርምም። ይልቁን ከዚያ የአስተሳሰብ እስራት ወጥቶ ሰው ሆኖ መገኘት ነው ቁም ነገሩ።

ከገዢዎች እስራት ነጻ ከመውጣት በፊት ከገዛ ኋላ ቀር አስተሳሰባችን ነጻ መውጣት ይኖርብናል። መሬት የረገጠ ለውጥ ሊያመጡ እውነተኛውን ሥራ እየሠሩ ላሉት አጋር መሆን ካቃተን፣ ቢያንስ አደናቃፊ ላለመሆን መጣር ነው።

በበፍቃዱ ኃይሉ

ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እያለሁ ፖለቲከኛ ከሆነውም ካልሆነውም ጋር በፖቲካ ጉዳዮች እንከራከር ነበር። ከክርክሮች በአንዱ ከተወሰኑ ሰዎች ጋር እኔ እንደሃይማኖት የማከርረውን “ሠላማዊ ትግል አልተሞከረም” እያልኩ እንደወትሮዬ ስሟገት የደረሰልኝ ብቸኛ ሰው ፍቅረማርያም አስማማው ነበር። ፍቅረ በሙግት ሲያጣድፉኝ የነበሩትን፣ እያንዳንዳቸውን “አንተ ሰልፍ ወጥተህ ታቃለህ? ፓርቲ ተቀላቅለህ ታቃለህ?…” እያለ ቀድመው አፋችን ላይ የሚመጡልንን የሠላማዊ ትግል እንቅስቃሴ የሚባሉትን ሁሉ ሲጠይቃቸው “አይ…” በማለት ይመልሳሉ። ከዚያ ፍቅረ “ብዙ ጊዜ ሠላማዊ ትግል አያዋጣም እያሉ የሚከራከሩት ምኑንም ያልሞከሩት  ናቸው” አለና ክርክሩን ቋጨልኝ።

ከዚያ ከፍቅረ ጋር ብቻችንን ስንሆን፣ “የምር የምታምንበትን  ነው የተናገርከው?” አልኩት። ግንቦት 7ን ለመቀላቀል ከብርሃኑ ተ/ያሬድ እና ከእየሩሳሌም ተስፋው ጋር ሲሄድ መያዙ ይታወቃልና።

እጅግ ሲበዛ የሚያስደንቀኝ  ትሕትና ያለው ፍቅረ፣ በተለመደ ትሕትናው ሊያስረዳኝ ሞከረ። “ለሠላማዊ ትግል ክብር አለኝ” ብሎ ነበር የጀመረው። “ቢሆንም…” በማለት ብዙ አስረድቶኛል። በተለይ መደራጀት በማይቻልበት ጥቂቶች ሠላማዊ ትግልን የመረጡ በግልጽ እየታዩ ለመኮርኮም ይመቻቻሉ አለኝ። ተለቅቄ እስክወጣ ክርክሯችን አልበረደም ነበር። ከዚያ በኋላ ግን አማራጩን ከሕይወት መርሔ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ ባልቀበለውም፣ ቢያንስ “የእነርሱን መረዳት አለብኝ?” በሚል ብዙ አስቤበታለሁ።

ምዕራፍ ፩ – ሦስቱ ወጣቶች በሠላማዊ መንገድ ላይ…

ለመጀመሪያ ግዜ እየሩስን በአካል የተዋወቅኳት እስር ቤት ውስጥ ነው። ‘ግራዚያኒ በትውልድ ሀገሩ የመታሰቢያ ኀውልት ሊሠራለት የማይገባ ነፍሰ–በላ ሰው ነው’ ብለው የተቃውሞ ሰልፍ ሲያደርጉ እኔ በዚያ’ጋ በአጋጣሚ ሳልፍ ፖሊስ እየደበደበ ሲያፍሳቸው አየሁ። ይቺንማ ፎቶ ማንሳት አለብኝ ብዬ ሦስት ፎቶ እንዳነሳሁ እኔም አብሬ ታሰርኩ። የሰማያዊ ፓርቲ እና የባለራዕይ ወጣቶች ነበሩ ሰልፈኞቹ። ፖሊሶቹ «እንፍታቸው፣ አንፍታቸው?»፤ «የት እናሳድራቸው?» ሲባባሉ ሦስት ጣቢያ እያዞሩን አስመሹን። እኔ በወቅቱ በፍርሐት ስርድ እነሱ ሌሎቹ በጀግንነት ይዘፍኑ ነበር። ማታ ላይ ብርዱ ይሁን ፍርሐቱ ሲያንቀጠቅጠኝ እየሩስ የመጣላትን ጋቢ አለበሰችኝ።…

በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ እያንዳንዳቸው ከ10 ጊዜ በላይ ታስረው ተፈትተዋል። ሁሉንም እስሮቻቸውን ጥፋተኛ ተብለውት አያወቁም። የሚታሰሩት አንዳንዴ “ወረቀት በተናችሁ”፣ አንዳንዴ ደግሞ “ዕውቅና ያልተሰጠው ሰልፍ ወጣችሁ” በሚሉና በሌሎችም ተልካሻ ሰበቦች ነው።

ታስረን እያለን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እየመጡ ይጠይቁን ነበር። ፍቅረ እና ብሬ አንድ ቀን ያለወትሯቸው ፊታቸው ላይ ተስፋ መቁረጥ በግልፅ በሚነበብበት ሁኔታ ሊጠይቁን መጡ። ሁለቱም ከከተማ ውጪ እንደነበሩ፣ እና ለምርጫ ዕጩ እየመለመሉ አንደከረሙ ነገሩን።

«እንዴት ነው ታዲያ?» በጉጉት ጠየቅናቸው።

«ተስፋ አስቆራጭ ነው» አሉ። «‘እኔን ዕጩ አድርጉኝ’ ብሎ ወጥሮ የያዘን ሁሉ አዲሳባ ስንደርስ ‘ይቅርብኝ፣ ይቅርብኝ’ ብሎ ይደውልልናል።»

«ምንድን ነው ችግሩ?»

«ችግሩማ ኢሕአዴግ ነው። ዕጩዎቻችንን እያስፈራሩ ራሳቸውን እንዲያገሉ እያደረጓቸው ነው። እምቢ ያሏቸውንም በየሰበብ አስባቡ እየሰረዙ ከግማሽ በላይ የሆኑትን አባሎቻችንን ሰረዙብን።»

ብርሃኑ «ከዚህ በኋላ በዚህ በኩል መጥተን የምንጠይቃችሁ አይመስለንም። ወይ በውስጥ እንገናኛለን፤» እንደሚታሰሩ ገምተዋል ብዬ ደመደምኩ። ወቅቱ ቅድመ ምርጫ እንደመሆኑ እስር ብርቅ አልነበረም።

ብርሃኑ ፖለቲካ ሲያወራ አንጀቴን ያርሰዋል። ቀረብ ብለው ሲያዋሩት የተቃዋሚውንም የኢሕአዴግንም ድክመት ያለስስት መተቸት ያውቅበታል።
ከዚያ በኋላ አልመጡም። ቆይተን መታሰራቸውን ሰማን። መጀመሪያ እንደወትሮው ዓይነት እስር መስሎን ነበር። ጉዳዩ ሌላ መሆኑ የገባን ዝርዝሩን ስንሰማ ነው። በአካል መልሰን የተገናኘነው ከማዕከላዊ ወደ ቂሊንጦ ሲዛወሩ ነው።

እኔ፣ አጥናፉ ብርሃኔ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዘላለም ወርቅአገኘሁ እና ሌሎችም የነበርንበት ዞን 2 የተመደበው ፍቅረማርያም ነበር። ፍቅረማርያም የግለሰብ አጀንዳ የሌለው ሲበዛ ትሁት ወጣት ነው። የሱን ትህትና የሚፎካከር ያገኘሁት አብርሃ ደስታን ብቻ ነው። ፍቅረ የሚታገለው በሚንቀለቀል ነገር ግን ለውለታው ምላሽ በማይፈልግ የወጣትነት ስሜት ነው።

ምዕራፍ ፪ – ሦስቱ ወጣቶች በፍርድ ቤት ክርክር…
(ያልተሞከረውን ሙከራ)

ልጆቹ ትግል ላይ በቂ ልምድ ስላላቸው ሲያዙ ሌሎች እንደሚያደርጉት ወደ ክህደት አልሄዱም። «ሠላማዊ ትግል ላይ ያለን እምነት ስለተቀየረ፣ የቀድሞ ፓርቲያችንን ሰማያዊን ለቀን፣ የግንቦት ሰባትን የትጥቅ ትግል ለመቀላቀል እየሄድን ነበር» አሉ። ይኸው ክስ ሆኖ ተመሰረተባቸው።

መዝገባቸው አራት ሰዎች ይዟል።
1ኛ፣ ብርሃኑ ተ/ያሬድ
2ኛ፣ እየሩሳሌም ተስፋው
3ኛ፣ ፍቅረማርያም አስማማው
4ኛ፣ ደሴ ካህሳይ

ደሴ ካህሳይ ወደኤርትራ ሊያሻግራቸው የነበረው ሰው ነው። እነብርሃኑ ፍርድ ቤት «ድርጊቱን ፈፅማችኋል ወይስ አልፈፀማችሁም?» ሲላቸው የሰጡትን መልስ ነው ‘ያልተሞከረውን ሙከራ’ የምለው።

«ድርጊቱን ፈፅመናል፤ ግን ጥፋተኞች አይደለንም» አሉ።

ከዚህ በፊት በግንቦት ሰባት ተጠርጥረው ያመኑ እና በዚያው የተቀጡ እስረኞች ገጥመውኛል። ሆኖም «ድርጊቱን ፈፅመናል። ጥፋተኞች ነን» ነበር የሚሉት።

«ምን አስባችሁ ነው?» አልኩት ፍቅረን።

«ግንቦት ሰባት በእኛ እምነት አሸባሪ ቡድን አይደለም። ነፃ አውጪ ቡድን ነው። ልክ የፀረ–ሽብር አዋጁ ሠላማዊ ትግልን እያደናቀፈ ነው ይሰረዝ እንደምንለው ሁሉ፣ የግንቦት ሰባት ‘አሸባሪ ነው’ የሚለውም እንዲሰረዝ ፍ/ቤቱን በሕጋዊ አካሄድ መሞገት እንፈልጋለን» አለኝ።

«እና በዚህ መንገድ ተከራክራችሁ እና ረትታችሁ ነፃ እንወጣለን የሚል እምነት አላችሁ?» የኔ ጥያቄ ነበር።

«ጉዳዩ በዚህ ክርክር ነፃ መውጣት አለመውጣት አይደለም። እኛ የምናደርገው ክርክር አንደኛ መንግሥት ሠላማዊ ትግሉን ሆነ ብሎ ሠላማዊ ወዳልሆነው ሜዳ እየገፋው እንደሆነና ለዚህ መከሰስም ካለበት ራሱ መንግሥት መከሰስ እንዳለበት፤ ሁለተኛ ግንቦት ሰባት የገዢው ፓርቲ እንጂ የሕዝብ ጠላት አለመሆኑን ለማሳየት መሞከር ነው ዓላማችን» አለኝ። ይህንን ስናወራ የነበረው እዚያው ቂሊንጦ እያለሁ ነበር። አሁን ተከላክለው ነፃ እንዲወጡ በ14ኛው የፌ/ወ/ችሎት ተበይኖባቸው የመከላከያ ምስክሮችን ለማስደመጥ ለመጋቢት 22, 2008 ተቀጥረዋል።

«እህ ምን አሰባችሁ?» በማለት የእስር ጓዶቼን ልጠይቃቸው ቂሊንጦ የሄድኩ ጊዜ ፍቅረን ጠየቅኩት።

ፍቅረ «ማንኛውንም በሠላማዊ ትግል የተሰማራ ሰው በሙሉ ከቻልክ ለኛ እንዲመሰክርልን ጥሪ እንድታደርግልን እንፈልጋለን» አለኝ። «እንዴ?» አልኩኝ ድንግጥ ብዬ። «ይሄማ እንዴት ሊሆን ይችላል። በሠላማዊ ትግል ውስጥ ያለ ሰው እኮ የናንተ ተቃዋሚ ነው። የተሳሳተ መንገድ ነው የሚከተሉት እያለ እንዴት ምስክር ይሁኑን ትላለህ?» አልኩት።

የሰጠኝ መልስ ባጭሩ እንዲህ የሚል ነው።

«እኛ የምንፈልገው ሠላማዊ ታጋዮች በሠላማዊ ትግል ውስጥ የገጠማቸውን ፈተና ለፍርድ ቤቱ እንዲያስረዱልን ብቻ ነው። ይህ መንግሥት ሠላማዊ ትግል እንዲያበቃለት መንግሥት ራሱ መንስኤ እየሆነ እንደሆነ ያሳይልናል። ቀሪውን ማስረዳት የኛ ድርሻ ነው።»

ፍቅረ በተጨማሪም ስርዓቱ ራሱ ለነሱ ውሳኔ እያደረገ ያለውን ኢ–ሕገመንግሥታዊ ዘመቻ አንድ ባንድ የሚሞግቱበት ስትራቴጂ እንዳላቸው ነገረኝ። ነገርዬው ፈረንጆቹ ‘ጁዲሻል አክቲቪዝም’ የሚሉት ሕግን መሠረት ያደረገ አክቲቪዝም ዓይነት መሆኑ ነው። እኔ በግሌ ወጣቶቹ የትግል ስትራቴጂ መቀየራቸውን አልወደድኩላቸውም ነበር። እስር ክፉ አጋጣሚ ቢሆንም፣ አጋጣሚውን ወደዕድል በመቀየር፣ ውጤቱ እንደጠበቁት ቢሆንም ባይሆንም  በሠላማዊ የትግል ስትራቴጂ (በጁዲሻል አክቲቪዝም) ራሳቸውን ለማስፈታት (ወይም አጭር ፍርድ ለመቀበል) ሳይሆን መንግሥትን ለሞገት በመወሰናቸው ደስ ብሎኛል።

በእኔ እምነት ከሠላማዊ ትግሉ ወጥቶ የኃይሉን መቀላቀል ለኢሕአዴግ እጅ መስጠት ነው። እስከዛሬ ደክመው እጅ የሰጡትን ሁሉ እየጠቀሰ የሚያሳጣው ኢሕአዴግ ነበር። አሁን ግን በነብርሃኑ ተ/ያሬድ መዝገብ የተከሰሱት ወጣቶች ‘ለዚህ ያበቃኸን አንተው ነህ’ እያሉ ኢሕአዴግን ይከሳሉ።

***
ብርሃኑ፣ እየሩስ፣ ፍቅረ እና ደሴ ከታሰሩ እነሆ ልክ አንድ ዓመታቸው ዛሬ።

More than 100 towns (with population more than 5,000) in Oromia have witnessed protests; more than 140 people were killed; and, more than 5000 people were arrested following the ongoing Oromo protests. Yet, it seems the protests are limited in Oromia region and didn’t show any sign of dispreading to other regions.

It is a serious issue but no political analyst seemed to be seriously concerned about it. Will the protest grow to be Ethiopia-wide? Is there even a need for it to be? If so, how? I will try to raise similar questions with my own answers. My hope is you will proceed in elaborating it.

Will Oromo Protests Continue?

Oromo protests are not only about the Addis Ababa expansion plan. As many Oromo civil rights activists are explaining, the protests are about anonymous self-administartion of Oromia, proprotional representation of its people in Federal administration, upraisal of Afaan Oromo to Federal working language status and etcetra. Therefore, lone-cancellation of the master plan would not stop the protests.

Harrassment, intimidation, mass arrest and killing are traditional instruments of Ethiopian government to stop social movements. In Oromo protests, however, this system had been applied against protesters in 2014 but failed to prevent explosion of the protests again for the second time in far more strength. This is an implication for that it continues even further regardless of government actions to silence them. Thus, we can conclude that the protests will continue but (in my opinion) their success will be dependent of two reasons: (1) they have to stick with non-violence startegies; i.e. they have to avoid any chance of turning the protests to violence; (2) the protests have to be coordinated not only intraregionally (within regional subdivison) but also interregionally (with other regions small, on and off protests).

Should Oromo Protests Continue?

There is no consensus among scholars as to what kind of social movement will result in grievances resolved. However, most scholars agree, the more popular a social movement gets, chances are more for it to succeed. It is in this understanding that many are seeking the protests in Oromia to dispread to the rest of regions in Ethiopia.

In addition, land grab – the primary cause of the current protests – is even worse in some regions such as Gambella. Liberal opposition groups have been blaming the constitution, which disgranted ownership rights of land from individuals, for not giving land owners the bargaining power over the land they till. Therefore, these groups, at least until Article 40 of the constitution gets amended to this regard, oppose the expansion of Addis to Oromia region. Moreover, there are other groups who are in continuous disagreement with the authoritarian regime of Ethiopia. Ethiopian muslims, who for the past four years non-violently resisted reported regime interference in religious affairs, are one example. TPLFites supermacy has been a disappointment of everyone for the past two decades. Everybody agrees democratization has declined backwards. Civil societies, free press, and the right to freely associate and demonstrate are weakened. Only a contested economic growth spared EPRDF led government from a total dark image.

All the above reasons make up the need for a coordinated, continued, Ethiopia-wide protests to be held for either the government will open doors for improvement or it will be changed by the will of the supreme people.

Do Ethiopians Protest?

Two scholars (whose name I forgot to mention) have two contrasting models of protest. (see pic.) The first model argues that social movements are high in either closed or open systmes; the assumption is that when a system is closed people need a scape, so they protest. When it is open, people see hope to get what they want through protests. Either way they protest. The other model (numberd two in the pic.), argues that people protest when a system is not open nor closed but lies in the middle. The assumption for this is that if a system is open, then there is no need to protest and if the system is closed, there is no way to. Emperical researches are said to support model two. It is in authoritarian regimes that people usually protest where the n-curve reaches its maximum peak.

Ethiopian government fits authoritarian regimes definition. It is founded in democratic principles according to the written constitution and have the structure to allow that. Practically, it is totalitarian system with extremely limited legitemacy and accountability. Therefore, it is a matter of time that all the rest Ethiopians, along with their Oromo brothers join in the protest.

There are, however, conditions to head to Ethiopia Protests starting from Oromo Protests:

1). Getting settled with Hagos vs. Tolla issue: while symbolizing inequality in simple terms, it is also important to recognize all individuals in an ethnic group can not be categorized in the same basket with elites who exploit the ethnic group for their own interest;

2) Establishing an anonymous and diversified activists’ group that leads protests: DimtsachenYisema (the online group that leads Ethiopian Muslims protests) is a good example. This assumed group, its leaders preferebly living abroad, plans peaceful strategies, creates public awareness, coordinates nation-wide movements and keeps the pace of the protest according to sought possibilities.

በውቀቱ ብዙዎቻችሁ እንደምታውቁት ሰው መኮርኮር ይችላል። የተማረው ሳይኮሎጂ ነው። ሳይኮሎጂ የሳቅ ስስ ብልት የት እንደሆነ አስተምሮት ይሆን እላለሁ። ነገር ግን ማሳቅ የጀመረው ትምህርቱን ከመጨረሱ በፊት ስለሆነ ብቻ ሳይሆን ሌሎች ሳይኮሎጂስቶች ሲያስቁ ስላልገጠመኝ በዚህ ረገድ ግንኙነት (co-relation) መፈለጌን አቋርጫለሁ።

በውቀቱን እንደ ኮሜድያን አልቆጥረውም [ነበር]። እንደዛ እንድቆጥር የተገደድኩበት አንድ ጊዜ ቢኖር ሀብቴ ከሞተ በኋላ ሀብቴን ተክቶ ሲመጣ ነው፤ ደረጄና በውቄ ነገር ሁኖ። እዚያ ላይ በውቄ ሀብቴን ተክቶ መምጣቱ ከቀልዶቹ የተሻለ ያስቅ ነበር፤ የተሻለ። በውቀቱ ያንን ሚና ደግሞ ላይመለስበት ባደባባይ ቃል ገብቷል።

በውቀቱ ፈላስፋ ነው፤ ኮሜድያን አይደለም። በነገራችን ላይ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋም በውቀቱን ፈላስፋ ነው ይላል። “ስንት ፕሮፌሰሮች ሁለት ክላስ የሚያሰተምሩበትን ሐሳብ እሱ በሁለት መሥመር ቁጭ ያረገዋል፣” በማለት፦
ሉላዊነት

“የጋራችን ዓለም፣ የጋራችን ሰማይ
የብቻችን ሕመም፣ የብቻችን ስቃይ።”

***

“አገር ድንኳን ትሁን ፣ ጠቅልዬ የማዝላት
ስገፋ እንድነቅላት፣ ስረጋ እንድተክላት።”

***

“ከተመኙ ላይቀር ወንዝነት መመኘት፣
አገርን ሳይለቁ ሰው አገር መገኘት።”

በራሪ ቅጠሎች ላይ የመጀመሪያዋ ጽሑፍ ትመስለኛለች በሕይወት ላይ የሚስቅባት ገፀ–ባሕሪይ አለ። ሕይወት ግን ዝም ብላ የምታስቅ እንዳልሆነች የልቦለዱ መጨረሻ ይተርካል። በመጨረሻው መጽሐፉ (መውጣትና መግባት) መግቢያ ላይ ደግሞ፣ ግጥም ተርጉሞ እንደመግቢያ አስቀምጧል። ታዲያ ዘነበ ወላ አዲስ አድማስ ላይ መጽሐፉን ሲተቸው (መጽሐፉ እንደበፊቶቹ ሲሪዬስ አይደለም ብሎ በማሰብ ይመስላል) “ተመልሰህ ግባ በወጣህበት በር” ብሎ ነበር ትችቱን የቋጨው (ከመግቢያ ግጥሙ ስንኝ ተውሶ)። የበውቀቱ መግቢያ ግጥም አሁን በቃሌ እንደማስታውሳት እንዲህ ትላለች፣

“በወጣኒነቴ በድሜዬ አፍላ ጀምበር፣
የሊቅ የጣዲቁን ሐተታ ቁም ነገር፣
አዘወትር ነበር፣
እና ምን ተረፈኝ?
ተመልሼ ወጣሁ፣ በገባሁበት በር።”

ወጥቶ ከሆነ እንኳን ወጣ። ውጪው በጣም ሰፊ ነው። በውቀቱ ደሞ ሲሪዬስሊ የማትወስደንን ተፈጥሮ ሲሪዬስሊ የማይወስድ፣ ለጥፊና ካልቾዋ የማያለቅስ ጸሐፊ ነው (ቢያንስ እኔ እንደተረዳሁት)። በውቀቱ ለኔ የዘመናችን ‘አይከን’ ነው። በለበጣ የሚመለከተንን ዘመን በተመጣጣኝ ለበጣ የሚመክትልን አሽሙረኛ። የኛ ማርክ ትዌይን፣ ወይም የኛ ቮልቴር ነው – በውቀቱ ስዩም!

የበውቀቱ ግጥሞች (በተለይ የኗሪ አልባ ጎጆዎቹ) የሐዘን እንጉርጉሮ ይበዛባቸዋል። ያኔ ተረከዙ የተበሳ ጫማ አድርጌ አዲስ አበባን ስዞር እነሱን በቃሌ እየወጣሁ ነበር ዕጣ ፈንታን እተች የነበረው። ሎሬት ፀጋዬ «ወንድ ልጅ ብቻውን ነው የሚያለቅስ» ሲል፣ በውቀቱ ደግሞ፣

“እምባ ታዛዥ ሆኖ የሚገደብበት፣
ያባት ቅኔና ቀን አለፈ እንደዘበት” እያለ ከውነቱ ያጋፍጠናል።

በሳት ዳር ሐሳቦች ስብስቡ “ከንፍገት እጦትን ማካፈል ይሻላል” ብሎ በፈገግታ ሲመጣ፣ እኔም ዓለምን በሽሙጥ ፈገግታ መመልከት ጀምሬ ነበር። በውቀቱ ከጉርምስና ወደጉልምስና ሳዘግም እንደ ሳውንድ ትራክ ተከትሎኛል። የኔን ትውልድ የሚወክል አይከን ነው የምለውም በዚህ መመዘኛ ነው። ዓለም ሲሪዬስ ሲሆኑላት ሲሪዬስ እንደማትሆን አሳይቶኛል። “የፀጋዬ ቤት ከፀጋዬ በፊት” ብሎ ሲል ዛቻ፣ “እግር አልባው ባለ ክንፍ” ብሎ ሲል ቡጢ ነው የገጠመው። የተሻለው ሽሙጥ ነው። የገባው ቁም ነገሩን ይጨብጣል፤ ያልገባው ስቆ ያልፋል። መሳቅ፥ መሳቀቅን ተካ።

እንደ በውቀቱ በቃላት የሚቀናጣ ባለቅኔ የለም። “ለካስ ያባቶች faith ፌዝ ብቻ ነበረ” እያለ የማይተዋወቁትን ቃላት ድንገት ማዛመድ የሚችለው እሱ ብቻ ነው። በውቀቱ የዶ/ር እጓለ ምናባዊ ሥልጣኔ ቢሰፍን የሚገኘው ውጤት ነው። የአገር በቀል ዕውቀትን ከምዕራባውያኑ ጋር ያዋሃደ ሰው። ስትፈልጉ ከቅኔ ቤት ወጎች፣ ስትፈልጉ ከአቴና ሰማይ ላይ ፊሎዞፊያን ጎትተው ባወረዱ ሰዎች ወግ ያጨዋውታችኋል።

ከቁምነገር መጽሔት እስከ ሮዝ (አዲስ ጉዳይ) መጽሔት ድረስ ያሉ ጽሑፎቹን ደጋግሜ በማንበብ «ጽሑፎችህን ካንተ የበለጠ አውቃቸዋለሁ» ወደሚል ትምክህት ደርሼ ነበር። ተነፈስኩ እንጂ። አሁን ደሞ፣ ፌስቡክ ላይ መጥቷል። እንደ ኗሪ አልባ ጎጆዎቹ ዘመን ሰዎች ጎጆዎቹን መሬት ላይ ቀልሰው መሬት ላይ ብቻ ተጋበዙልኝ ብለው ድርቅ እንደሚሉት ጸሐፍት ሆኖ አልቀረም። ትውልዱ ፌስቡክ ላይ ሲወጣ እሱም ጎጆውን እዚያው ቀልሷል። ጎጆው ውስጥ በቀልድ እያስመሰለ የዘመናችንን እውነት ይተርክልናል። ጎጆውን መቀለስ በጀመረ ጊዜ እኔም እዚሁ ሰፈር ነበርኩ። ጓዙን ጠቅልሎ ፌስቡክ በከተመ ጊዜ ግን “እረፍት” ላይ ነበርኩ። ስለዚህ አሁን “እንኳን ደህና መጣህ” ብለው ረፈደብህ አልባልም። እዚህ ሰፈር ለማይደራደሩብህ አድናቂዎችህ ታስፈልገናለህ።
———
ግጥሞቹን በቃሌ ስለወጣኋቸው ቢሳሳቱ አያገባኝም።

“ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት ምንድን ነው? ማበሳጨትን ካላካተተ፣ ሕልውና የለውም፡፡” ~ ሰልማን ሩሽዲ
፩ – ማበሳጨት

‹‹በመስከረም ወር 1997፣ ዢላንድስ ፖስተን የተባለ የዴንማርክ ጋዜጣ ነብዩ መሐመድ ላይ የሚሳለቁ ካርቱኖችን ይዞ ወጣ፡፡ የዚህ ሕትመት ዜና በመላው ዓለም እንደተሰማ በየቦታው ያሉ ሙስሊሞች ቁጣቸውን በአደባባይ መግለጽ ጀመሩ፡፡ የተቃዋሚዎቹ ምክንያቶቻቸው ሁለት ናቸው፤ አንደኛ፣ ነብዩ መሐመድን በምስል መግለጽ በእስልምና ሃይማኖት አይፈቀድም የሚልና፤ ሁለተኛ፣ ካርቱኖቹ በጥቅሉ እስልምናን እና ሙስሊሞችን ከሽብር ጋር አቆራኝተው ይገልጻሉ የሚል ናቸው፡፡  ሠላማዊ ሰልፎችና ሕዝባዊ ተቃውሞዎች በጋዜጣው አዘጋጆች እና በዴንማርክ መንግሥት ላይ ተቀሰቀሰ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዳንዶቹ ሕይወት እስከመቅጠፍ የዘለቀ አመጽ የተቀላቀለባቸው የተቃውሞ ሰልፎች ነበሩ፡፡ ካርቱኖቹ ግን በመላው ዓለም በሚገኙ በሌሎች ጋዜጦች ላይ ለዢላንድስ ፖስተን ጋዜጠኞች የሞራል አጋርነት ለማሳየት በሚል ሰበብ ድጋሚ ታትመው ይበልጥ ተሰራጩ፡፡›› (Paul Sturges, 2006)

ሌላ ምሳሌ እንውሰድ፡፡ አንድ ወንድ “‹ሴቶችን ማስተማር የአገርን ሀብት ማባከን ነው፤ ስለዚህ ሴቶችን ማስተማር ካለብን የቤት አያያዝ፣ ምግብ ማብሰል እና ልጅ አስተዳደግ እናስተምር እንጂ ሌላ ‹የነጭ ኮሌታ› ሥራ የሚያስይዝ ትምህርት ማስተማር የለብንም› የሚል አስተያየት ሲሰጥ በቴሌቪዥን ተላለፈ፡፡ ይህን ተከትሎ የከተማው ሴቶች የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ፡፡ ወንድ አሽከርካሪዎች የሚነዷቸውን መኪኖች ሰባበሩ፡፡ ወንዶችን እያሳደዱ ደበደቡ፡፡” በዚህ የፈጠራ ታሪክ ውስጥ የአስተያየት ሰጪው ሐሳብ ሴቶቹን አበሳጭቷቸው ይሆናል፡፡ ነገር ግን ለአመጹ እነርሱን አነሳስቷቸዋል ብሎ መደምደም ከባድ ይሆናል፡፡ አማጺዎቹ ሴቶች ስሜታቸውን መቆጣጠርና ሐሳቡን በሐሳብ መመከት ካልቻሉ ድክመቱ የነርሱ የራሳቸው ይሆናል፡፡

የዴንማርክ ፍርድቤት የፈረደውም፣ እኔ በላይኛው አንቀጽ አመጸኞቹ ሴቶች ላይ የሰጠሁትን ዓይነት ብይን ነው፡፡ “እርግጥ ነው ስዕሎቹ የተወሰኑ ሙስሊሞችን ማበሳጨታቸው አይካድም፤ነገር ግን የካርቱኖቹ ዓላማ ሙስሊሞችን ማንኳሰስ አልነበረም›› ብሏል ፍ/ቤቱ፡፡ ሲያብራራውም፣ “ስዕሎቹን አመጽ ወይም ቦንብ የመወርወር ድርጊት በእስልምና ሥም እየተደረገ ነው፤” በሚል መረዳት የካርቱኖቹ ተመልካቾች ድርሻ ነበር ብሏል፡፡ የዴንማርክ ፍርድ ቤት ብይን ለካርቱኒስቶቹ ያደላ ቢመስልም ካርቱኒስቶች ራሳቸው ላይ ቅድመ ምርመራ እንዲያደርጉ ክስተቱ አስገድዷቸዋል፡፡ ነገር ግን የአንድ ሐሳብ (expression) አንባቢ፣ ተመልካች ወይም አድማጭ የራሱን ስሜት መቆጣጠር ድርሻ የራሱ መሆን ካልቻለ ቢያንስ የሆነ ሰውን የማያበሳጭ ሐሳብ ማፍለቅ በጣም አስቸጋሪ ስለሚሆን፣ ‹በነጻ› ቀርቶ ሐሳብን መግለጽ የሚባለው ጉዳይ ራሱ አይኖርም፡፡

 አምና የፈረንሳዩ ‹ሼርሎ ሆብዶ› መጽሔት ባወጣቸው ካርቱኖች ተበሳጭተው ጋዜጠኞችን፣ ካርቱኒስቶችን እና ፖሊሶችን የገደሉ ፅንፈኛ-ሃይማኖተኞች ጉዳይም ሊታይ የሚችለው በዚሁ ዓይን ነው፡፡ ፅንፈኞቹ የእነርሱን እሴት ያላከበረ፣ በእነርሱ እሴት መሠረት መቀጣት አለበት የሚል እርምጃ ነው የወሰዱት፡፡ ክስተቱ ለሐሳብ ነጻነት አራማጆች መርዶ ነው፡፡ አጋጣሚውን ተከትሎ ተቀጣጥሎ የመጣውም ውይይት ሰዎች ራሳቸውን በራሳቸው ሳንሱር እንዲያደርጉ የሚያስፈራራ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አጋጣሚው የኢትዮጵያውን ጨምሮ ለአምባገነን (authoritarian) መንግሥታት ፕሮፓጋንዳ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል፡፡ ሐሳብ እንዴት መገደብ እንዳለበት ክስተቱን አስታክከው ደስኩረዋል፡፡ እነዚህ መንግሥታት ሊያስተውሉት ያልፈለጉት ነገር ቢኖር ከዴንማርክ እስከ ፓሪስ የተከሰተው ነገር ጋዜጠኞች ሐሳባቸውን በነጻነት ሲገልጹ የመንግሥት ከለላ እንደሚያስፈልጋቸው እንጂ ሐሳባቸውን በበነጻነት ከመግለጽ እንዲቆጠቡ የሚመክራቸው አልነበረም፡፡
ሌሎችን ማበሳጨት የተወሰኑ የማኅበረሰብ ክፍሎች ላይ ወይም ግለሰቦች ላይ ሲከሰት ከሞላ ጎደል ከላይ ባየነው ሁኔታ ሊያልፍ ይችላል፡፡ ችግሩ የተበሳጨው አምባገነን መንግሥት (የመንግሥት ባለሥልጣናት) ሲሆኑ ነው፡፡ እነ ኤልያስ ገብሩ (አምሳሉ ገ/ኪዳን ዕንቁ መጽሔት ላይ በሚያዝያ ወር 2006 የጻፈውን ጽሑፍ ተከትሎ ጅማ ዩንቨርስቲ አካባቢ በተነሳው የተቃውሞ ብጥብጥ ሳቢያ) የተከፈተባቸው የአመጽ ማነሳሳት ክስ መታየት የሚኖርበት በዚህ ዓይን ነው፡፡ መንግሥት ጸሐፊዎቹንም፣ ለጽሑፉ የጽሑፍ ምላሽ በመስጠት ፈንታ በኃይል የጸሐፊውን ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት የተቃወሙትን፣ ሁለቱንም በክስ በማስተናገድ ጉዳዩን ለመፍታት እየጣረ፣ ጉዳዩ እስካሁን በእንጥልጥል ነው፡፡ ተመስገን ደሳለኝ ሦስት ዓመት የተፈረደበት የመንግሥት ባለሥልጣናትን የማያስደስት አልፎም የሚያበሳጭ ጽሑፍ ስለጻፈ ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ ክሱ ከሽብር ወደ ‹በጽሑፍ አመጽ ማነሳሳት› የተቀየረው በተመሳሳይ ምክንያት ነው፡፡ ተጠያቂነት የሌለባቸው የመንግሥት ባለሥልጣናት በሐሳብ ሲበሳጩ ውጤቱ የከፋ ይሆናል፡፡

፪ – የጥላቻ ንግግር እና አመጽ ማነሳሳት

በ1987 ሩዋንዳ በዓለማችን የቅርብ ጊዜ ታሪክ ውስጥ ሰቅጣጭ የሆነውን ዜና ለዓለም አርድታለች፡፡ በ100 ቀናት ውስጥ 800 ሺሕ ያህል ሰዎች ተጨፍጭፈዋል፡፡ በጭፍጨፋው 70 በመቶ ቱትሲዎች (ወይም 20 በመቶ ሩዋንዳውያን አልቀዋል)፡፡ የጭፍጨፋው መነሾ ላይ የታሪክ ባለሙያዎች ሙሉ ለሙሉ ባይስማሙም በጎሳ ስም አመጽ እንዲቀጣጠል ያደረገው ግን የሚዲያ የጥላቻ ንግግር እንደሆነ ብዙዎቹ ይስማማሉ፡፡ ከዘር ጭፍጨፋው ዓመት ቀድሞ የተቋቋመው ሬዲዮ-ቴሌቪዥን ሊብሬ ደስ ሚል ኮሊንስ (አር.ቲ.ኤል.ኤም.ሲ) ዋነኛ ሚና ተጫውቷል፡፡ አንዳንድ ጥናቶች በዘር ጭፍጨፋው የዚህን ሚዲያ ተቋም ሚና እስከ 10 በመቶ ያደርሱታል፡፡ ሬዲዮው በጣም ተወዳጅ ከመሆኑ የተነሳ ከዜጎቹ ጋር በአጭር ጊዜ ለመዋሃድ በቅቷል፡፡ ይህ ሬዲዮ ነበር ቱትሲዎችን “በረሮ” ብሎ መጥራት የጀመረው፡፡ “በረሮዎቹን ደግሞ ማስወገድ አስፈላጊ ነበር፡፡” አለበለዚያ ችግር ያስከትላሉ፡፡ ሬዲዮው በተጨማሪም “በረሮ” ብሎ የጠራቸውን ዜጎች ማስወገድ ስለማስፈለጉ ብቻ ሳይሆን እንዴት መወገድ እንዳለባቸው ጭምር ተንትኗል፡፡ የጭፍጨፋው ፈፃሚዎች በአንድ እጃቸው ቆንጨራ፣ በሌላኛው ሬዲዮ ይዘው እንደነበር ሪፖርት ተደርጓል፡፡

በሩዋንዳ ጭፍጨፋ የነበረው ሬዲዮ ብቻ አልነበረም፡፡ ጋዜጣም የበኩሉን ተጫውቷል፡፡ ካንጉራ የተባለ ሳምንታዊ ጋዜጣ ‹የሁቱ ዐሥርቱ ትዕዛዛት› የተሰኘ ተወዳጅ ጋዜጣ ነበረው፡፡ ጋዜጣው በይፋ ሁቱዎች ከቱትሲዎች ጋር ምንም ወዳጅነት እንደሌላቸው አውጇል፡፡ ጠላት ናቸው በሚል ሚስቶች በባሎቻቸው፣ ጎረቤት በጎረቤቱ ላይ በዚህ የማንነት ጠላትነት ላይ ተመሥርተው እንዲነሱ አድርጓል፡፡

የሩዋንዳ ሚዲያዎች የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ እና ዘመቻ ውጤቱ እልቂት ሆኗል፡፡ ሚዲያዎቹ ወደዘር ጭፍጨፋ የደረሱት በሦስት ደረጃዎች ነው፤ መንግሥት ሚዲያውን በተሳሳተ መንገድ ተጠቅሞበታል – በጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ለዘር ጭፍጨፋ ማዘጋጃ አድርጎታል (1)፣ በጭፍጨፋው ወቅት አመፁን አቀጣጥሏል (2)፣ ከዚያም የጥፋቱ መጠን በትክክል ለሕዝብ እንዳይደርስ አድርጓል (3)፡፡

አሁን የሩዋንዳ መንግሥት ያንን መጥፎ ጠባሳ የጣለበትን ታሪክ ለማጥፋት በማሰብ የሁለቱንም ጎሳዎች ማንነት ክዷል፡፡ በሩዋንዳ አንዱ ሌላውን የእከሌ ጎሳ አባል ነው ብሎ በይፋ መናገር አይፈቀድለትም፡፡ ይህንን የዘር ጭፍጨፋን በማፈን ፈንታ ሐሳብን የመግለጽ ነጻነትን ያፈነ እርምጃ እንደሆነ አጥኚዎች ይከራከራሉ፡፡ (Yakaré-Oulé (Nani) Jansen, 2014) ለሩዋንዳ መንግሥት ግን ጉዳዩ ግራ አጋቢ ነው፡፡ ለሩዋንዳ መንግሥት ብቻ ሳይሆን ለብዙዎች ሌሎችን እስከ ማበሳጨት በሚደርሰው ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት፣ በጥላቻ ንግግር እና በአመጽ ቅስቀሳ መካከል ያለውን ልዩነት መረዳት አስቸጋሪ ፈተና ይሆንባቸዋል፡፡

ኢትዮጵያም ጭምር የፈረመችው የሲቪል እና ፖለቲካዊ መብቶች ዓለምዐቀፍ ቃልኪዳን እንደሚለው “ማንኛውም ዓይነት በብሔር፣ ዘር፣ ወይም ሃይማኖት ላይ የተመሠረተ የማግለል፣ ጠላትነት ወይም አመጽ የሚያነሳሳ መልዕክት በሕግ መከልከል አለበት፡፡” ሆኖም አንድ ንግግር ወይም መልዕክት የጥላቻ ሊባል የሚችለው የትኛው ደረጃ ላይ ሲደርስ እንደሆነ መግባቢያ የለም፡፡

አስቀድመን ባየናቸው ምሳሌዎች የሚዲያ እና አመጽን ግንኙነት ስንመለከት፤ አበሳጭ የተባሉ ይዘቶችን ይዘው የወጡ የሕትመት ውጤቶች፣ አመጽ አልቀሰቀሱም፡፡ ይልቁንም የተቃውሞ አመጽ ተቀስቅሶባቸዋል፡፡ የሩዋንዳው የዘር ጭፍጨፋ ደግሞ በተቃራኒው አመጹ የተካሄደው በሚዲያዎቹ የጥላቻና ጥፋት ስብከት መሪነት ነው፡፡ በነዚህ ሁለት ምሳሌዎች መካከል ያለውን ልዩነት መረዳት ከባድ ላይሆን ይችላል፡፡ የአመጽ ቅስቀሳ ከመደረጉ በፊት ለመከላከል ያንን ዓይነት አዝማሚያ ያለውን የሚዲያ ተቋም ቀድሞ መቆጣጠር ግን ከባድ ይሆናል፡፡ የማይቻል ግን አይደለም፡፡ ይህንን የሚቻል-ከባድ የመንግሥት ሥራ ክፍተት የሚረዱ አምባገነኖች ሚዲያን (ወይም ሐሳብን የመግለጽ ነጻነትን) ለማፈኛ እንደምክንያት ይጠቀሙበታል፣ እየተጠቀሙበትም ነው፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት በብሔር ላይ ያተኮሩ አንዱን የሚያጠለሹ፣ ሌላውን ተበዳይ የሚያደርጉ የቁርሾ ታሪኮችን እንዲያውም በበጎ ሲመለከታቸውና ሲታገሳቸው ይታያል፡፡ የገዢው ፓርቲ አመሠራረትም ሆነ አቋቋም የብሔር በዳይ-ተበዳይ ግንኙነትን አጠፋለሁ በሚል ሥም ስለሆነ እነዚህ ዓይነቶቹ ትረካዎች የተስማሙት ይመስላል፡፡ ነገር ግን መንግሥት ለእነዚህ አደገኛ አዝማሚያ ላላቸው ሐሳቦች/ጽሑፎች ያለውን ትዕግሥት ቅንጣት ታክል እንኳን ስርዓቱን ለሚተቹት የለውም፡፡ ይህም የሚያስገነዝበው መንግሥት ለሐሳብ ነጻነትም፣ ይሁን ሕዝቦች ላይ ለሚደርሰው አመጽ እንደማይጨነቅ፤ ይልቁንም ለሥልጣኑ ብቻ እንደሚሳሳ ነው፡፡ ሐሳብን በመግለጽ ነጻነት እና አመጽ በመቀስቀስ መካከል ያለው ልዩነት ጠርቶ በሕግና መመሪያ እንዲደነገግ የማይፈልገውም ለዚያው ነው፡፡

“ማንም ከብስጭት የመጠበቅ መብት የለውም፡፡ ይህ መብት እስከዛሬ ባነበብኳቸው ድንጋጌዎች ሁሉ ላይ የለም፡፡ ከተበሳጫችሁ፣ የራሳችሁ ችግር ነው፤ እንደእውነቱ ብዙ ነገሮች ብዙ ሰዎችን ያበሳጯቸዋል፡፡” ~ አሕመድ ሰልማን ሩሽዲ!

This article is published on Addis_Gets magazine, on Tahsas 3, 2008 issue. 


የሆነ ጊዜ የሰማኋት ቀልድ ትዝ አለችኝ፤ አንዳንድ የተቃዋሚ ተወካዮች ፓርላማ ውስጥ በነበሩበት በዚያ በደጉ ጊዜ ነው አሉ፡፡ አንድ ተወካይ የሻዕቢያ መንግሥት ላይ ሊደረግ ስለሚገባው እርምጃ ሲናገሩ እንዲህ አሉ፤ “አሁኑኑ ገብተን ድምጥማጣቸውን ማጥፋት አለብን፡፡ አለበለዚያ ካደሩ አይቆረጠሙም፤ እነዚያ ወያኔዎችም ያኔ ሲመሠረቱ ሳንጨፈልቃቸው ዝም ብለናቸው ነው ዛሬ አናታችን ላይ…” አሉና ያሉበት ቦታ ትዝ ሲላቸው ድንግጥ ብለው ወደአቶ መለስ መቀመጫ አማተሩ፡፡ አቶ መለስ በጥሞና ያዳምጣሉ፤ ተወካዩ እንደደነገጡ “…ልጨርሰው ወይስ ትጨርሰኛለህ?” አሉ ይባላል፡፡
የሕወሓት/ኢሕአዴግ ወታደሮች አዲስ አበባ ደርሰው “ሲቪል” መንግሥት ከመመሥረታቸው አስቀድሞ “እኩይ” ናቸው በሚል ሲቃወማቸው የነበረ እና እስካሁንም ስክነቱ ያልተለየው አክቲቪስት ታማኝ በየነ ነው፡፡ የታማኝ የአክቲቪስትነት ሪከርድ ከኮሜዲያንነቱ የሚመዘዝ ነው፡፡ በቀልዶቹ ቢጀምርም አሁን ግን በጣም ‹ሲሪዬስ› ነው፡፡ አሁን እነቪኦኤ፣ ዶቸ ቬሊ፣ ኢሳት በየቤቱ እንደሚደመጡት ከደርግ ማክተሚያ ቀደም ብሎ ብዙ ሰው በየቤቱ ‹ድምፂ ወያነ›ን በድብቅ ያደምጥ ነበር፡፡ የፕሮፓጋንዳ ሚዲያዎች አመል ነውና ያው ውሸታቸው አይጣል ነው፡፡ ታዲያ ታማኝ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ቀርቦ የምሩን ሲቀልድ ‹እዚህ ቦታ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር፣ እዚያ ቦታ ደግሞ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር ደመሰስን ይላሉ፡፡ ሲደመር ግን ይሄን ያክላል፡፡ ቆይ እኔ የምለው ወያኔዎቹ የሚደመስሱት ጦር ከጠቅላላ ጦሩ በለጠ እኮ፤ ከየት እያመጡ ነው የሚደመስሱት?› ዓይነት ቀልድ ተናግሮ አላገጠባቸው፡፡ ከዚያ በድምፂ ወያነ መልስ ተሰጠው፤ “ቁጥሩን አዲስ አበባ ስንደርስ እናወራርዳለን” የሚል፡፡ ዛቻ የሽፍትነት ዘመንም አመል ነበረች፡፡
ግንቦት 20/1983 – ኢሕአዴግ አዲስ አበባን ሲረግጥ፣ ሲ ኤን ኤን ካነጋገራቸው ሰዎች አንዱ ታማኝ በየነ ነበር፡፡ “በመሣሪያ ተከበናል፣ ምንም ሠላም የለም…” የሚል ነገር ለጋዜጠኛው ሲነግረው ይታያል፡፡ ታዲያ ታማኝ ሁኔታውን በቀልድ ሲያስታውስ “ጓደኞቼ ከውጪ ደውለው ‹ሲ ኤን ኤን› ላይ አየንህ ሲሉኝ፣ ወዲያውኑ እንግሊዝኛዬ እንዴት ነበር?” አልኳቸው ይላል፡፡
ታማኝ ከአዲሱ ስርዓት ጋር አብሮ መኖር በማይችልበት ሁኔታ የተቀያየመው፣ ካልተሳሳትኩ የወቅቱ ባለሥልጣናት፣ እነታምራት ላይኔ በተገኙበት ስታዲዬም ውስጥ በቀለደው ቀልድ ነው፡፡ እንደማስታውሰው ቀልዱ በማንነት ላይ የተመሠረተ እና ለኢሕአዴግ የማንነት ብያኔ የማይበገር ዓይነት ቀልድ ነው፡፡

ፍቃዱ ማሕተመወርቅ፣ የቀድሞዋ ዕንቁ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ነበር፡፡ በመጽሔትና ጋዜጦች አከፋፋይነትም ይታወቃል፡፡ አሁን መጽሔቱ ተዘግቶ “በታክስ ስም” ፍርድ ቤት እየተመላለሰ ይገኛል፡፡ ፍቃዱ ነጻው ፕሬስ ሲጀመር ጀምሮ ምኅዳሩን ያውቀዋል፤ እናም “እናንተ በደጉ ጊዜ ነው የመጣችሁት” እያለ ይቀልድብኛል፡፡ ያኔ (ማለትም የመጀመሪያው አንቀጼ ላይ ‹ደግ› ባልኩት፣  ለፍቃዱ ግን ‹ክፉ› ግዜ) አንድ ሰው ስርዓቱን የሚያስቀይም ንግግር ሲናገር፣ እንዳሁኑ በሕግ ሥም ፍርድ ቤት አይመላለስም፣ የደረሰበት ይጠፋና ከአራት አምስት ወር በኋላ ተመልሶ ይመጣል፡፡ እንዳይሞት እንዳይሽር ተቀጥቅጦ ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ከዚያ ወዲህ ያሻሻልነው ነገር ቢኖር ፍርድ ቤት የመቅረብ ዕድል መፈጠሩ ነው ማለት ነው፡፡ የሆኖ ሆኖ ይህን ያነሳሁት ታማኝ ላይ የደረሰውም እንዲህ ያለው ነገር ነው ለማለት ነው፡፡
ታማኝ ተሰደደ፡፡ ብዙዎች ሲሰደዱ አቅላቸውን ያጣሉ፡፡ የሀገር ቤት ናፍቆት መመለስ ካለመቻሉ ጋር ተደማምሮ ይሁን፣ የሄዱበት አገር ኢሕአዴግ የማይደርስባቸው ከመሆኑ በተጨማሪ የሚያዩት ነጻነት ስለሚያስቀናቸው አላውቅም ብቻ ጠርዝ ይይዛሉ፡፡ ጥቂቶች ብቻ ሚዛናቸውን በጥፍራቸው ቆንጥጠው ይቆማሉ፡፡ ታማኝ ለኔ ከጥቂቶቹ አንዱ ነው፤ ያውም በረዥም ቆይታ ይህንን ማስመስከር የቻለ፡፡ ታማኝ አሁን አክቲቪዝሙን የሚሠራው ብዙ ጊዜ የቪዲዮ ማስረጃዎችን እያቀረበ ነው፡፡ ቪዲዮዎቹን ዩቱዩብ ላይ ሳያቸው በክምችቱ እቀናለሁ፡፡ ለረዥም ጊዜ የአገር ቤት ጉዳይን እየተከታተሉ፣ ማስረጃዎችን እየሰበሰቡ የመቆየት ፅናት የገቡበትን ጉዳይ ርዝመት እና ክብደት ከመረዳት ይመነጫል፡፡
የማስረጃ ነገር ከተነሳ አይቀር፣ አሁን እነ ታማኝ ማስረጃ ዶት ኮም (masreja.com) የተባለ ድረአምባ ፈጥረዋል፡፡ ድረአምባው በአሁኒቷ ኢትዮጵያ ውስጥ በሕግ የበላይነት ፈንታ ራሳቸው ከሕግ የበላይ ሆነው ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎች ላይ ማስረጃ የሚሰበሰብበት ነው፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ እኔ በይቅርታ አምናለሁ፤ እስከዛሬ አዲሱ ያለፈውን እየቀጣ የመጣበት ዑደት ቢያንስ የእኛ ትውልድ ላይ ቢቆም እያልኩ እመኛለሁ፡፡
ይህንን በተመለከተ ጓደኛዬ ሶሊያና “ይቅርታ ከፍትሕ ጋር መጋጨት የለበትም” ብላ ሞግታኛለች፡፡ ልክ ነች፤ በወቅቱ የሰጠችኝን ምሳሌ ከወቅታዊው ሁኔታ ጋር አዋህጄ ልናገር፤ “#OromoProtests ላይ ልጇ የተገደለባት እናት የስርዓት ለውጥ ቢመጣ እና ለገዳዩ ወታደር ይቅርታ አድርጊለት ብትባል ፍትሕ ተደረገልኝ ብላ ታምናለች?” በወቅቱ፣ ሶሊም እኔም ጥያቄውን ከመጠየቅ በቀር መልስ መስጠት አልቻልንም፡፡ እርግጥ ነው ልጁ የሞተው የመጣው ለውጥ እንዲመጣ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በምሳሌያችን መሠረት አወዛጋቢው ማስተር ፕላን ቢሰረዝ እንኳን ልጁ የለውጡ እሸት ተጋሪ ላይሆን አልፏል፡፡ ይቅርታ ለአገሪቱ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ያስፈልግ ይሆናል፤ የቤተሰቡን አባል ወይም ወዳጁን ላጣው ግለሰብ ግን ፍትሕ ሆኖ ይሰማዋል ማለት አይቻልም፡፡ የሆነ ሆኖ፣ ለይቅርታውም ቢሆን ማስረጃውን መሰብሰብ አስፈላጊ ነው፡፡ አጥፊው ጥፋቱን እንዳይክድ፣ ይቅርታ ጠይቁኝ ባዩም በማስረጃ እንዲሞግት፡፡
ማስረጃ መሰብሰብ ሕገ-ወጥ መስሏችሁ የምትፈሩ ካላችሁ አትሳሳቱ፡፡ ሕጋዊ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት ራሱ በፀረ-ሙስና ኮሚሽን በኩል አላግባብ የተገኘ ሀብት ካለ በሚል የባለሥልጣናቱን ሀብት ምንጭ ሳይቀር የማጣራት ማንዴት አለው፡፡ ቁርጠኝነቱ ስለሌለ አልተሳካላቸውም፤ እኛ ግን ይሳካልናል፡፡ በየቀኑ ከታችኛው እርከን (ወረዳ) እስከ ላይ ድረስ የምንጠየቃቸውን ጉቦዎች፣ ባለሀብቱና ባለሥልጣናቱ (ሁለቱም አንድ ናቸው) ኢ-ርትዓዊ በሆነ መንገድ የሚያካብቱትን ሀብት፤ ከትላልቆቹ እስከ ትናንሾቹ ሹመኞች በሕዝብ ላይ የሚፈፅሙትን ግፍ፤ ትንንሽሽም፣ ትልልቅም ሠላማዊ ተቃውሞዎች በተነሱ ቁጥር በንፁሐን ዜጎች ነፍስ ላይ የሚሰነዘሩትን የኃይል እርምጃዎች የሚያጋልጡ ማስረጃዎች ባገኘን ቁጥር ለማስረጃ ዶት ኮም በመላክ ለኢትዮጵያችን የወደፊት መልካም ዕጣ ፈንታ ሲባል እንዲከማቹ የበኩላችንን እናድርግ፡፡ ማስረጃዎቹን መሰብሰቡ ሌላው ቢቀር አጥፊዎቹን ስለሚያስፈራቸው በደላቸውን ሊያላሉልን ይችላሉ፡፡

ቪቫ ላ ታማኝ!!!

‪#‎Ethiopia‬ #FreeZone9Bloggers 
ለተሻለች ኢትዮጵያ የተሰባሰቡ ያገባናል ያሉ ወጣቶች ከተሰባሰብን ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ጦማራችንን በይፋ ካወጅን ዛሬ ድፍን ሶስተኛ አመታችን ሆነ፡፡
እንደ ዜጋም፣ እንደ አገርም ያለመታደል ሆኖ ብዙ ብለን ተባብለን፣ የምንማማርበት ጊዜ እንዲኖረን አምባገነኖች አልፈቀዱምና ፣ የጠበበው ነጻነት ተዳፍኖብን ሥራችንን ሳይሆን እስራችንን መቁጠር ከጀመርን ደሞ አንድ ዓመት ሞላን፡፡ ራሳችንን እና የተቋቋምንበትን ስራችንን ረስተን እስራችንን ብቻ በምናስብበት ሰዓት ጎግል ልደታችንን ስላስታወሰን እናመሰግናለን፡፡
ይህ ሶስተኛ አመት በእስርና በስደት ያለን ዞን9ኛውያን ሳንነጋገር የምናስታውሰውና ወደኋላ ተመልሰን ሃሳባችንን የምናንጸባርቅበት አንደሆነ እናምናለን፡፡
ሶስቱን አመታት በሙከራችን በጥረታችን እንዲሁም በክፉ ጊዜያት አብራችን ስለቆያችሁ እናመሰግናለን፡፡
አጋርነታችሁ አይለየን ፣ ስለሚያገባን እንጦምራለን፡፡

ከዞን9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች
ጊዜው በጣም ይነጉዳል፡፡ ሀላፊነት የማይሰማው ስርዓት የገዛ ዜጎቹን ዕድሜ በእሳት ይማግዳል፡፡ ሚያዚያ 17/08/2006 ዓ.ም በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንድንውል የተደረግነው ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን እና ሶስት ጋዜጠኞች ይሔው ከታሰርን ድፍን አንድ የእስር አመት ቆጠርን፡፡ መለስ ብለን ስናየው አጭር በሚመስለው ዓመት ውስጥ የሆነውንና የታዘብነውን ጠቅለል አድርገን ለማካፈል እንሞክራለን፡፡ይህ የእኛ ገጠመኝ እና ትዝብት፣ የሃሳብ ልዩነትን ማስተናገድ የሚከብደው መንግስት እስካለን ድረስ የነበረ እና የሚኖር ስለሆነ የሁሉም ‹የኅሊና እስረኛ › ገጠመኝ እና ትዝብት ሊሆን እንደሚችል አስታውሱልን፡፡
‹እንዳይችሉት የለም . . .›
ከያለንበት ቦታ በዘመቻ መልክ ተይዘን የፌደራል ወንጀል ምርመራ ዘርፍ (በተለምዶ ‹ማዕከላዊ›) በገባንበት ቅፅበት ነበር ሥርዓቱ እንዴት እንደሚሰራ ከውስጡ መመልከት የጀመርነው፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ስርዓቱ ውጪ ሆነን ከምናውቀው የባሰ እንጂ የተሻለ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ ለምርመራው የተያዝነውን ‹‹ተጠርጣሪዎች ›› የሚያቆዩባቸው ክፍሎች መሰረታዊ የሆነውን ሰብዓዊነትን ከግንዛቤ ውስጥ ያላስገቡ እና ሕግ የማያውቃቸው ይመስላሉ፡፡ ተዘግተው በሚውሉና በሚያድሩ ክፍሎች ውስጥ ተበታትነን ታጉረን በቀን ሁለቴ (ለአስር ደቂቃዎች) መፀዳጃ ቤት እንድንሄድ(ተፈጥሮን በቀጠሮ እንድንቆጣጠር ) እንገደድ ነበር፡፡ ‹የፀሃይ ብርሃንም› በቀን አንዴ ለአስር ደቂቃ እንቃመስ ነበር፡፡ይህምየሚሆነው የእኛን ‹መብት› ለማክበር ታስቦ ሳይሆን በአሳሪዎቻችን ‹በጎ ፈቃድ› ነው፡፡ ክፍሎቻችን ውስጥ ሆነን የሰማናቸውና ያየናቸው በታሳሪዎች (inmates) የሚወሩት እና በገዛ አይናችን የምንታዘባቸው የሰቆቃ ታሪኮች ብቻ ናቸው፤ ምንነቱ ያልታወቀ ነገር ‹‹እመን››በሚል የማይቀጣ የለም፡፡ ማዕከላዊ ውስጥ እረፍት ብርቅ ነው፤ የካቴና ድምፅ በተቅጨለጨለ ቁጥር ‹‹ማነው ባለተራ›› የሚል ጭንቀት ሁሉንም ሰው ሰቅዞ ይይዛል፡፡ የትኛው ተረኛ ወደ ‹ምርመራ› ክፍል ተወስዶ ይደበደብ ይሆን? የሁሉም እስረኛ ጥያቄ ነው፡፡
ሁላችንም ለጥያቄ ‹ምርመራ› ክፍሎች ውስጥ በተመላለስንባቸው ጊዜያት ሰብአዊ ክብራችንን እንድንዘነጋ እንገደድ ነበር፡፡ ፀያፍ  ስድቦችን የመርማሪዎቻችን አፍ መፍቻ የሆኑ ይመስል ከንፈራቸው ላይ ተንጠልጥለዋል፡፡ጥፊ፣ ካልቾና ስፖርታዊ ቅጣቶች የእለት ቀለቦቻችን ነበሩ፡፡ ሴቶች ሊደረግልን የሚገባ ጥበቃ ቀርቶ ሴትነታችንን መቀጣጫ የሚያደርግ አበሻቃጭ (abusive) ‹ምርመራ› ተደርጎብናል፡፡ ‹የምርመራ› ስዓቱ ገደብ የለውም ጠዋት፣ ከሰዓት፣ ማታ እና ሌሊት ሊሆን ይችላል፡፡ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ከእንቅልፍ ተቀስቅሶ ወደ ‹ምርመራ› ክፍል መወሰድ እና የደንቡን ተደብድቦ መምጣት የተለመደ ነው፡፡ ለነገሩ ማዕከላዊ የቆየ ሰው የሚታሰርባቸው ክፍሎች የተፈጥሮ ብርሃን የማያስገቡ እና ለ24 ሰዓታት በቂ የሆነ የኤሌክትሪክ ብርሃን የማያገኙ በመሆናቸው መምሸት እና መንጋቱን እንኳን ለማወቅ በፖሊስ መነገርን ይጠይቃል፡፡ የመጀመሪያዎቹን ሶስት የእስር ወራት በዚህ ሁኔታ አሳለፍን፡፡
‹የመርማሪዎችን› አካሄድ በመመልከት በጋራ የተረዳነው አንድ ነገር ቢኖር የተጠረጠርንበት ተጨባጭ ወንጀል ወይም ማስረጃ ያልነበረ መሆኑን ነው፡፡ ሆኖም መጀመሪያ ‹በተጠረጠርንበት› ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በአመፅ እና በዛቻ ለማፍረስ እና ማኅበረሰብ ሚዲያን ለአመጽ ለመጠቀም የመሞከር ወንጀል ወይም ኃላ በተከሰስንበት የሽብርተኝነት ድርጊትን ለመፈፀም የማሴር፣ የማነሳሳት፣ የማቀድ፣ የመዘጋጀትና የመሞከርን ወንጀል ከእኛው አፍ (በሃሰትም ቢሆን) በጉልበት ለመስማት ‹የመርማሪዎቹ› ቁርጠኝነት ወደር ያልነበረው መሆኑን ነው፡፡ እንዲያም ሆኖ ቤታችን፣ ቢሮአችን፣ ኮምፒውተሮቻችን ፣ስልኮቻችንና ቃላችን ሁሉ ተፈትሾ የተገኘው ማስረጃ እንኳንስ ክስ ሊያቋቁም ቀርቶ የተገላቢጦሽ የእኛን ንፅህና የሚመሰክሩ ሆኑ፡፡ ይሁን እንጂ ሕግ የማይገዛው አሳሪያችን ከ15 ዓመት እስከ ሞት ሊያስቀጣ የሚችል ክስ አቀረበልን፡፡ጉዳዬን ይበልጥ አስገራሚ የሚያደርገው ደሞ በምርመራው ወቅት አንድም ቀን የሽብር ተግባር እና አላማቸውን በማስፈጸም የተከሰስንባቸው ድርጅቶች አንዳቸውም አለመጠቀሳቸው ነው ፡፡
ክሱን ተከትሎ ወደ አዲስ አበባ የቀጠሮ ማረፊያ ቤት (ወንዶች ወደ ቂሊንጦ ሴቶች ወደ ቃሊቲ) ተላክን፡፡ ማረፊያ ቤቶች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና የሚንስትሮች ምክር ቤት ያወጡላቸው መተዳደሪያ አዋጅና ደንብ ያላቸው ሲሆን፤ ነግር ግን የሚገዛቸው ያልተፃፈ ሌላ ደንብ ነው፡፡ በተለይ ሴቶችን የሚያሳድረው የቃሊቲው የአዲስ አበባ የሴቶች የቀጠሮ ማረፊያ ቤት ገና ለገና ‹በሽብርተኝነት ወንጀል የተጠረጠርን› በመሆናችን ብቻ አግላይ አያያዝ በማድረግ የቀደመ ልምዱን ተግብሮብናል፡፡ ከሌሎች ተጠርጣሪዎች / ታራሚዎች በተለየ ሁኔታ የጠያቂዎቻችንን ስም ዝርዝር እንድንፅፍ በማስገደድ መብታችንን ሲገድብብን፣ የምንጠየቅበትን ሰዓትም በአዘቦት ቀን ከአስር ደቂቃ እና ቅዳሜና እሁድ ደግሞ ከ30 ደቂቃ እንዳይበልጥ አድርጓል፡፡ ጉዳዩን ለፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ብናቀርብም የማረፊያ ቤቱ አስተዳደር ‹ችግር የለም› በማለት እውነታውን በግልጽ ሲክድ ፍርድ ቤቱም ተባብሮት አጽንቶታል ፡፡ ፍትህን የሕግ የበላይነት ከፖሊስ እጅ እንዳጣነው ሁሉ በአያያዝ ረገድ ከማረፊያ ቤቱም ደጃፍ ልናገኘው አልቻልንም፡፡
ፍ/ቤቱ ‹እንደተጠርጣሪ› ለማረፊያ ቤቶቹ ያስረከበን በአደራ አቆዩልኝ ብሎ ቢሆንም፣ ማረሚያ ቤቱና የመብት ረገጣው ዋነኛ ተዋናዮች የሚመለከቱንግን ግን በጦር ሜዳ እንደማረኩት ግዳያቸው ነው ፡፡ እኛም በዚህና መሰል ለደህንነታችን ምንም አይነት ዋስትና በማይሰጥ አያያዝይህንን የመአት ዓመት ችለን አንድ ዓመት አስቆጥረናል፡፡
ምን ያሟግተናል?
በግልፅ የአሳሪያችንን መልካም ፈቃድ በወገንተኝነትና በታማኝነት በሚያገለግሉ ግለሰቦች የሚመሩትን የፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ዘርፍ (ማዕከላዊ) ‹የወንጀል ምርመራ ቡድን› እና በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ‹ገለልተኝነት› ተሸማቀን ስናበቃ የተጋፈጥነው አንበሳውን  የፍትህ ስርዓታችንን ነው፡፡
ወንጀልን ሊያቋቁም የሚችል ምንም አይነት ማስረጃ በሌለበት በወንጀል መጠርጠራችንና መከሰሳችን ከሁሉም ቀዳሚው በደል እንደሆነ ይሰማናል፡፡ ነገር ግን ስለፍትህ አውርተናል ጠይቀናል ተከራክረናልና የኖርንበትን ታላቅ አላማ እኛው ፈልገን የፍትህ በርን እያንኳኳን እንገኛለን፡፡ ‹‹ለምን ተጠረጠርን?›› ‹‹ለምንስ ተከሰስን?›› ብለን ፍትህን ከመሻት ራሳችንን ሳናቅብ የቀረበብን ክስ እንደ ክስ ሊቆም የማይችል እንደሆነ ሕጋዊና ሙያዊ መቃወሚያ አቅርበን ፍርድ ቤቱም ‹ተቀብዬዋለሁ ግን አልተቀበልኩትም› በማለት ልንረዳው ያልቻልነውን ውሳኔ አስተላልፏል፡፡ ከእስራችንም በፊት የምንታወቅበትን የአገሪትዋን ህግ በመጠቀም መብቶቻችንን የመጠየቅን ሂደት አጠናክረን የምንገፋበት ተቋማቱ ገለልተኛ ናቸው ብለን ስለምናምን ሳይሆን ከተቋማቱ ጀርባ ላለው ፍትሕ እና ህግ የበላይነት ያለንን ቁርጠኛነት ለማሳየትም ጭምር ነው፡፡
ከሳሻችን አለኝ የሚለውን ‹ማስረጃ› በከፊል ከእኛ ከተከሳሾች ደብቆ እንኳን የተባለውን ‹ማስረጃ› ለማድመጥ የአንድ አመት ጊዜ መጠበቅ ነበረብን፡፡ የዘገየ ፍትሕ እንደተነፈገ ይቆጠራል መባሉን ከሳሻችን እንደሚያውቅ ብናውቅም እኛ ግን የዘገየውን ‹ፍትሕ› እንኳን ለመጠየቅ የሚያስችልትዕግስት አላጣንም፡፡
አሁንም ፍትሕ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ዓይነተኛ መለያ ቀለም ነው ብለን እናምናለን፡፡ ፍትሕ ይኖር ዘንድ ገለልተኛ ተቋማት መኖራቸው ደግሞ የግድ ነው፡፡ ተቋማት ለተቋቋሙበት ዓላማ ከመኖር ይልቅ ታማኝነታቸውን ለስርዓቱ ሹማምንት ማድረግ ሲጀምሩ ፍትሕ አስቸጋሪ ፈተና ውስጥ ይገባል፡፡ ፍትሕ እኛ በታሰርንባት ኢትዮጵያ ይሕ ፈተና እንደገጠማት ይሰማናል፡፡ እንግዲህ የኛ ተስፋና ጥበቃም ከዚህ እውነት የሚመነጭ ነው፡፡
ወንጀላችንን ፈልገን ማግኘት አልቻልንም በህግ ፊት ንጹህ ነን ነገር ግን በሚያሳዝን ሁኔታ ይሕ ንፅሕናችን መቼና እንዴት እንደምንፈታ አይነግረንም፡፡ አንድ ነገር ግን እርግጠኞች ነን፡- እውነት ከኛ ጋር መሆኗን፡፡
በተስፋ የሚያቆመን . . .
እኛን ከአገራችን ብቻ ሳይሆን ከመላው ዓለም የዴሞክራሲ ቤተሰብ ጋር ያስተሳስረናል ብለን የምናምነው ዕሴት ሐሳብን በነፃ የመግለፅ ነፃነት ላይ ያለን ፅኑ እምነት ነው፡፡ ሰዎች ሀሳባቸውን ያለምንም ጣልቃ ገብነትና ፍርሃት መግለፅና መደማመጥ ሲችሉ አገራችንን ጨምሮ በዓለማችን ያሉ ማህበራዊ ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮችን መቅረፍ የሚችሉ ሀሳቦችና መነሳሳቶች መፍጠር ይችላሉ የሚል እምነት ከመታሰራችንበፊትም ይሁን በኋላ በውስጣችን አለ፡፡ የታሰርነውም ይህንን ተፈጥሮአዊ ነፃነታችንን ለመጠቀም ሙከራ ማድረግ ስንጀምር ነው፡፡ በየትኛውም አምባገነናዊ ሥርዓት ውስጥ እውነትን ለጉልበተኞች መናገር ዋጋ ያስከፍላል፡፡ እኛም ሐሳባችንን በነፃነት ስለመግለፅ እየከፈልን ያለነው ዋጋ የማይከብደን የነገይቱ ኢትዮጵያ ከዛሬይቱ ኢትዮጵያ የተሻለች ትሆናለች የሚል ተስፋ በማድረጋችን ነው፡፡
የሚያበረታን . . .
የመታሰራችንዜና ከተሰማ ጀምሮ ብቻችንን አልታሰርንም፡፡ ብዙዎች አኛን ከከለለን አጥር ውጪ አብራችሁን ታስራችኋል፡፡ ስለዚህ የእስርቤት ጌጥ የሆኑት የመረሳትና ተስፋ የማጣት ስጋቶች እንዳይጎበኙን ያደረገንና በብርታት ያቆመን የእናንተው በእሳት የተፈተነ አብሮነት ነውና ሁላችሁም ምስጋና ይገባችኋል፡፡
እምነታችን እዳ ሆኖባችሁ ከታሰርንበት ደቂቃ አንስቶ የመንፈስም፣ የአካልም ዕረፍት ሳያሻችሁ እየደከማችሁ ላላችሁ ቤተሰቦቻችን፣ በፈተናችን ሰዓት ሕመማችንን አብራችሁ ለታመማችሁ ወዳጆቻችን (friends indeed)፣ ከታሰርንበት ጊዜ ጀምሮ ንፅህናቸንን ተረድታችሁ ጉዳያችንንእንደ ጉዳያችሁ እየተከታተላችሁ ላላችሁ እና የመንፈስ ድጋፋችሁ ላልተለየን አገር በቀል እና አለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሃን፣ ሰብአዊነትናየዴሞክራሲ ተቆርቋሪዎች ስለድካማችሁ ምስጋናችን የበዛ ነው፡፡ የማረፊያ ቤት ቆይታችን አዲስ አይነት የህይወት ልምድ የምናገኝበትናየምንማርበት ይሆን ዘንድ አብራችሁን በማረፊያ ቤት የነበራችሁ/ያላችሁ እህቶቻችንና ወንድሞቻችን እናንተም ምስጋናችን ይድረሳችሁ፡፡ እንዲሁም ይህን በሕግ አግባብ ያልተመሰረተ ክስ በሕግ አግባብ እንዲቋጭ ያላሰለሰ ጥረት እያረጋችሁ ያላችሁት ጠበቆቻችንና ሌሎቻችሁም. . . ምስጋናችን ከልባችን የፈለቀ ነው፡፡ ሁላችሁም የምንበረታው በእናንተ ነውና እጅግ በጣም እናመሰግናለን፡፡

#Ethiopia  #FreeZone9Bloggers  #FreeEdom  #FreeTesfalem  #FreeAsemamaw 

አጥናፍ ብርሃኔ 
ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ( ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት) በተለይ
– ሳጅን ምንላድርግልህ
-ታደሰ ወይም ጥጋቡ ( የሽፋን ስም )
– ኢንስፔክተር አሰፋ
– ም/ሳጅን መኮንን
– ኢንስፔክተር ገብሩ
ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – ሚያዝያ 17 እስከ ሃምሌ 11 /2006 አም

የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ በተለይ ቢሮ ቁጥር 5.፣ 32

ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
– ታደሰ የተባለው መርማሪ ፓሊስ ያለምንም ምክንያት ምርመራ ክፍል ውስጥ እያነቀኝ በተደጋጋሚ “እውነቱን የማትናገር ከሆነ ሽባ ነው የምናደርግህ ፣ እኛ ለግለሰብ መብት አንጨነቅም” በማለት በጥፊ ሲደበድበኝ ነበር

– ሳጅን ምን ላድርግልህ የተባለ መርማሪ “ጦማር ምን ማለት አንደሆነ ተናገር” ሲለኝ ጦማር ማለት መጻፍ ነው ብለውም ፡።፡።”ምህጻረ ቃል ነው እያንዳንዷ ምጻረ ቃል ምን ማለት አንደሆነች ካልተናገርክ አንላቀቅም” በማለት ከግርግዳ ጋር እያጋጨ ደብድቦኛል፣ ከግርግዳ ማጋጨት ብቻም ሳይሆን ረጅም ሰአት ከአቅሜ በላይ የሆነ የአካል አንቅስቃሴ እየሰራሁ የተመረመርኩ ሲሆን ምራቁን እየተፋብኝ አጸያፊ ስድብ ሲሰድበኝ ነበር፡፡

– ግንቦት ወር ላይ ሳጅን ምን ላድርግልህ የተባለው መርማሪ “ ኢህአዴግን ለምንድነው ተችታችሁ የምትጽፉት ?” “ከአገር ውጪ የምትሄዱት የመንግሰትን ስም ለማጥፋት ነው አንጂ የአባይ ግድብ ቦንድ ለመግዛት አይደለም” በማለት እጄን ወደላይ አድርጌ አንድመረመር አንዲሁም ጆሮዬን እየጎተተ በጥፌ ሲደበድበኝ ውሏል፡፡ ከዚህ ቤት ደንቁረህ ነው የምትወጣው በማለትም ያስፈራራኝ ነበር፡፡ እየተፋብኝ አጸያፊ ስድብ እየተሰደብኩ አካላዊና ስነልቦናዊ ጥቃት ተፈጽሞብኛል፡፡

– በሰኔ ወር ኢንስፔክተር አሰፋ የሚባለው መርማሪ ሌሊት 6 ሰአት አካባቢ ጠርቶኝ አላማችሁን ካልተናገርክ ጭለማ ቤት ነው የምትገባው በማለት ከማስፈራራቱም በላይ ሌሎች እስረኞች ሲደበደቡ እና ሲጮሁ ሲያለቅሱ በማሰማት እነደነሱ አንዳትሆን በማለት ዛቻ ተፈጽሞብኛል።

– ሰኔ ወር ላይ ኢንስፔክተር ገብሩ የታሰርኩበት ክፍል ውስጥ በመግባት ወረቀት ጽፈሃል የሚል በውል በማላውቀው ምክንያት ከሌሎች እስረኞች ለይቶ በተኛሁበት በተደጋጋሚ ከባድ የእርግጫ ደብደባ ፈጽሞብኛል። ሲደበድበኝም ህዝብ ልታጫርስ ነው እያለ ነበር፣ አስካሁንም የዛን ቀኑን ድብደባ ምክንያት ነው ያሉትን ነገር አላውቀውም፡፡

– በማእከላዊ ቆይታዬ 4በ4 በሆነች ክፍል ውስጥ በቀን ሁለቴ ብቻ ለ15 ደቂቃ ወደውጪ በመውጣት ከአስር ሰው ጋር ተቆልፎብኝ ታሬያለሁ ፡፡ የመጸዳዳት እድልም ቀኑን ሙሉ አልነበረኝም ፡፡ በየቀኑ ከባድ የአካል አንቅስቃሴ መስራት የምርመራው አካል ነበር፡፡

– በሃምሌ ወር ከምሽቱ 2.30 አካባቢ ሳጅን ምንላድርግልህ ፣ ም/ሳጅን መኮንን እና ሌላ የማላውቀው መርማሪ በመሆን ጭንቅላቴን በሃይል ከግንብ ጋር በማጋጨት እና የኮምፒውተር ኬብል በማሳየት አንደምገረፍ በመንገር ሳጅን ምንላድርግልህ የተባለው መርማሪ ፓሊስ የጻፈው የእምነት ቃል ላይ በግዳጅ አንድፈርም ተገድጃለሁ፡፡

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው 

ኤዶም ካሳዬ
ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት እና የፌደራል ደህንነት መስሪያ ቤት አባላት መርማሪ ደስታ በዋናነት

ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – በተያዝኩባቸው ቀናት በሙሉ በተለይ ሚያዝያ 18 ,20, 21, 22, 23
የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ቢሮ ላይ
ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት

-መርማሪዬ ደስታ በተደጋጋሚ በጥፊ ይመታኝ ነበረ ሲሆነ ከዚህ ቤት የፈለግነውን ልናደርግሽ እንችላለን በአካል አትወጪም እያለ አስፈራርቶኛል

-የዞን 9 አባል አይደለሁም በማለቴ ፌቴን አዙሬ ከባድ የአካል አንቅስቃሴ የሰራሁ ሲሆን በተጨማሪም አላማቸውን ተናገሪ ሲለኝ የተለየ አላማ እንዳላቸው አላውቅም በማለቴ ሳታውቂ አንዴት አብረሻቸው ትውያለሽ ሸርሙጣ ብሎ በተደጋጋሚ ሰድቦኛል፡። ሌሎቹ መርማሪዎች አብረው ተቀምጠው በስድቦቹ ይስቁ ነበር

-ሌላኛው ተከሳሽ አጥናፍ መደብደቡን ፍርድ ቤት በመናገሩ አንቺ ትሞክሪውና ዋጋሽን ታገኛለሽ እኛ ፍርድ ቤት አያዘንም የግለሰብ መብትም አያሳስበንም ብሎኛል

-ጥጋቡ የሚባለው መርማሪ ምርመራ መሃል ደንገት በሩን ከፍቶ ገብቶ በጥፊ መቶኝ ይወጣ ነበር ( ስለምናወራው ጉዳይም ሆነ ስለምርመራው ሳይሰማ) እምቢ ካለችህ ልብሷን አስወለወቀህ ግረፋት ብሎ እኔን የተለመደውን ስድብ ሰድቦኝ ሄዷል

-በምርመራ ወቅት የዞን አባል ነኝ ብለሽ እመኚ ተብዬ ልብሴን አውልቄ ሙሉ እርቃኔን አንድመረመር ተገድጃለሁ ፡። በጥፊ እመታ የነበረ ሲሆን በዚህ ቀን ምርመራው ምሽት ላይ ጀምሮ እስከ ሌሊቱ 6 ሰአት ቆይቷል

-በተለምዶው ከምመረመርበት ቢሮ ውጩ አንደኛ ፎቅ አዳራሽ ውስጥ ለምርመራ ተወስጄ ልብሴን እንዳወልቅ እና የተለያዬ ለመናገር የሚከብዱ ስፓርታዊ አንቅስቃሴዎችን እንድሰራ ተገድጃለሁ፡፡ እንዲህ ከምትዋረጂ አመጽ ልናስነሳ ነበር ብለሽ ለምን አታምኚም እያለ ይመታኝ ነበር ፡፡ በጥፊው ተደጋጋሚነት የተነሳ ታምሜ ክሊኒክ ተመላልሻለሁ::

-በጋዜጠኝነት ሞያየ የተሳተፍኩበትን ስልጠናዎች ስናገር አንቺ ለምን ተመረጥሽ የኢቲቪ ጋዜጠኞች ለምን አይሄዱም አንቺ ለፈረንጅ ስለምትሰልዬ ነው ብሎኛል፡፡ በተጨማሪም ዞን9 ላይ የሚወጡት ጽሁፎች አንድ ገጠር ያለ ሰው ቢያነበው ለአመጽ የሚያነሳሳው ልማቱን የሚያጣጥል ነው ብሎ በተደጋጋሚ በጥፊና በካልቾ ተመትቻለሁ፡፡

-በተጨማሪም በተፈቺ እስረኛ ወደውጪ መልእክት ልከሻል በሚል ሰበብ ሌሊት ተጠርጬ በዱላ ሲዛትብኝ አርፍዷል

-በእስሩ ወቅት ከማህሌት ፋንታሁን ጋር ለብቻችን ከሰው አንዳንገናኝ ተደርገን ቆይተናል፡፡

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

ዘላለም ክብረት
ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት እና የፌደራል ደህንነት መስሪያ ቤት አባላት መርማሪ ታደሰ ወይም ጥጋቡ ( ስሙ በትክክል የማላውቀው) በተለይ መርማሪ ምን ላድርግልህ መርማሪ ጽጌ መርማሪ አብዱልመጂድ
ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – በተያዝኩባቸው ቀናት በሙሉ በተለይ ሚያዝያ 17፣ ሚያዝያ 22 ሚያዝያ 25 እና ግንቦት 9
የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ቢሮ ላይ
ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
– በታሰርኩነት ወቅት ህጋዊ የእስር እና የብርበራ ትእዛዝ አልነበረም፡፡ ህጋዊ ያልሆነ ፍተሻ ከ12 ሰአት በኋላ አታድርጉ ብልም የሚሰማኝ አላገኘሁም ፡። ፍተሻው በከፍተኛ ማስፈራሪያ የታጀበ ነበር፡፡ ፓሊስ ጣብያ እሄዳለሁ ብለህ እንዳታስብ ራስህን ለምትሄድበት ቦታ አዘጋጅ እያሉ ከፍተኛ ስነልቦና ጫና አድርሰውብኛል
– በመጀመሪያው ቀን ፍርድ ቤት ስንቀርብ ትምህርቴን አጠናቅቄ ላስረክበው ያዘጋጀሁትን የመመረቂያ ጽሁፍ ፓሊስ መያዙን እና ኮፒ አድርጌ እንዳስረክብ ይፈቀድልኝ ብዬ ስጠይቅ ፍርድ ቤቱም መብቱ ነው ብሎ ትእዛዝ ቢሰጥም ፓሊስ ትእዛዙን ተግባራዊ አንዲያደርግ ብጠይቅ የማዕላዊ ወንጀል ምርመራ ሃላፊ ኢንስፔክተር “ፍርድ ቤት እኛን አያዘንም“ ” የት ያለህ መሰለህ” ዳኛዋ ታስረክብልህ” አንዲሁም “አንዲህ አይነት ጥያቄ ካነሳህ እርምጃ ይወሰድብሃል” የሚሉ ንግግሮችን ተናገረውኝ አንጓጠውኛል በዚህም ምክንያት መመረቂያ ጽሁፌን ማስረከቤ ተሰናክሏል፡፡
– በምርመራ ወቅት በዙ አጻያፌ ስድቦችን እየተሰደብኩ የምመረመር ሲሆን ከነሱም መካከል “የነጭ ተላላኪ የነጭ አምላኪ አገር ሻጭ ከሃዲ “ የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡
– የዞን 9 አላማ ተናገር ካልሆነ ያሉንን የምርመራ መንገዶች ተጠቅመን እንድታወጣ እናደርጋለን የሚለው ማስፈራሪያ በተደጋጋሚ በምርመራ ወቅት የደረሰብኝ ነው
– የሰጠሁት ቃል ላይ እኔ ያላልኩትን ጨምረው በፍርሃት ጥፋተኛ ነኝ ብዬ አንድፈርም ከመገደዴም በላይ የበላይ አካል ተቀባይ አንዲሆን በሚል እየቀያየሩ በተደጋጋሚ አስፈርመውኛል፡፡
*ይህ ጽሁፍ ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

ተስፋለም ወልደየስ

ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ( ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት) መርማሪ የህይስ መርማሪ ጽጌ መርማሪ ታደሰ ( ስሙን እርግጠኛ ያልሆንኩት) 

ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት ማእከላዊ ምርመራ በቆየሁበት ጊዜ ሁሉ 
የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – ማእከላዊ ወንጀል ምርመራ

ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
-በውል በማላስታውሳቸው ቀናት እስከእኩለ ሌሊት ድረስ የቆየ ምርመራ ተደርጎብኛል
-ለ75 ቀናት በተለምዶው ሳይቤሪያ የሚባለው ቦታ በቀን 15 ደቂቃ ብቻ የጸሃይ ብርሃን ለማየት ተፈቅዶልኝ ከዚያ ውጪ ያለውን ጊዜ 24 ሰአት አንድ በር ተዘግቶብኝ ቆይቻለሁ፡፡
-አራት በአራት በሆነ በዚህ ክፍል ውስጥ ቁጥራቸው አስር ከሚደርሱ ተጠርጣሪዎች ጋር ጤናዬን ለከፋ አደጋ የሚያጋልጥ ሁኔታ ውስጥ ነበርኩ
-በእስር በቆየሁባቸው ቀናት በቀዝቃዛው ሳይቤርያ ውስጥ በማሳለፌ በከፍተኛ ቅዝቃዜው የተነሳ ለጤና ጉዳት እና ለበሽታ ተዳርጌያለሁ
-ከፍተኛ እና ከአቅሜ በላይ የሆነ የአካል እንቅስቃሴ ያደረኩ ሲሆን በምርመራ ወቅት በተደጋጋሚ እመታ ነበር
-በዚህም የተነሳ ከፍተኛ የስነልቦና ጉዳት ደረሰብኝ ሲሆን በስተመጨረሻም ያላልኩትን አለ ተብዬ ፣ የማላምንበት እና ያልፈጸምኩትን ጥፋተኛ ነኝ ብለህ ፈርም በመባሌ ለመፈረም ተገድጃለሁ

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው 

ናትናኤል ፈለቀ 

ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ( ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት) በተለይ ሳጅን ምን ላድርግልህ ፣ ም/ሳጅን አብተው 

ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – ሚያዝያ 22 ( ከምሽቱ 2 ሰአት ገደማ)፣ ሚያዝያ 23 ከጠዋቱ 4 ሰአት፣ ግንቦት 6( ከምሽቱ 3 ሰአት ገደማ)፣ ሚያዝያ 24 ከጠዋቱ 4 ሰአት እና ከሚያዝያ 22 እስከ ግንቦት 6/2006 ድረስ ባሉት ቀናት ከእሁድ በስተቀር 

የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ላይ ቢሮ ቁጥር 30፣ 32 በ1981 አም በተሰራው ህንጻ ላይ 2ተኛ ፎቅ በስተግራ ጥግ በኩል ያለ ቢሮ

ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
– በምርመራ ወቅት ዛቻ እና ማስፈራሪያ የደረሰብኝ ሲሆን በተጠራሁባቸው ቢሮ ውስጥ ሁሉ በጥፌ ተደብድቤያለሁ ፡፡ በጥፌ መመታት የተለመደ ነበር ፡። በተደጋጋሚ ክፍተኛ ስፓርት የሰራሁ ሲሆን በቀን 10 ደቂቃ ብቻ የፀሃይ ብርሃን እያየሁ በጠባብ ክፍል ውስጥ ያለምንም ተፈጥሮ ብርሃንና መጸዳጃ ለ 76 ቀናት ቆይቻለሁ፡፡

– ጫማዬን አውልቄ በባዶ እግሬ አንድቆም ከተደረኩ በኋላ እግሮቼ ጣቶች ላይ መርማሪዎቹ በጫማቸው በሃይል በመርገጥ እግሬ ላይ ከባድ ድብደባ አድርሰውብኛል፡፡ ምርመራው እስኪጠናቀቅ ድረስም እጄ እንደታሰረ አናቴ ላይ አድርጌ እንድመረመር ተገድጄ ነበር፡፡

– የምሽት ምርመራዎች ወቅት በአብዛኛው ጊዜ እጄን ወደላይ አድርጌ እንድመረመር እገደድ ነበር ፡። ምርመራው ቀኑን ሙሉ የሚቆይ ሲሆን ምሽት እስከ ሌሊቱ ስድስተ ሰአት ድረስ ስፓርት በመስራት እና ፌቴን በማዞር እንድመረመር እገደድ ነበር፡፡

– ሰብአዊነቴን የሚነኩ ስድቦች ልክስክስ ፣ ውሻ መሳሰሉትን ስድብ በምርመራ ወቅት እሰደብ የነበረ ሲሆን አካለ ጎዶሎ ሆነህ ነው ከዚህ ቤት የምትወጣው ፣ ለግለሰብ መብት አንጨነቅም አንተን አንደፈለግን እነድናደርግ አሰራራችን ይፈቅድልናል የሚሉ ተደጋጋሚ ማስፈራሪያዎች ነበሩብኝ ፡፡

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

አቤል ዋበላ 
ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ( ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት) በተለይ
– ምን ላድረግልህ 
– ታደሰ ወይም ጥጋቡ ( የሽፋን ስም )
– ደስታ ወይም ሃሰን ( የሽፋን ስም)
– ዬሃንስ
– ፈይሳ
ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – ሚያዝያ 18(ከሰአት ከ8-10) ፣ ግንቦት 11 ( ከምሽቱ 2 ሰአት- ሌሊቱ 6 ሰአት) እና ሰኔ 26 ( ከምሽቱ 4 ሰአት -ሌሊቱ 7 ሰአት) እና በማእከላዊ ምርመራ በልዬ ሁኔታ በቆየሁባቸው 76 ቀናት
የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ላይ ቢሮ ቁጥር 5.፣ 32፣30 ፣ የስብሰባው አዳራሽ እና ከዋናው ህንጻ ተነቅሎ በሚገኝ ህንጻ ውስጥ በሚገኝ ጨለማ ክፍል
ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
– የተያዝኩበት ማግስት አቶ ምን ላድርግልህ የተባለ የምርመራ ክፍሉ አባል ብሄሬን ጠይቆኝ ኢትዬጲያዊ መሆኔን እና በተለያዬ ብሄሮች ስር ራሴን አንደማልገልጽ እና በጥቅል ኢትዬጲያዊ መባል አንደምመርጥ ነገርኩት ተነስቶ ድብደባ ጀመረ ፡፡ በጥፌና በእርግጫ በተደጋጋሚ መታኝ፡፡ ሌላው መርማሪ ንግግራችንን ያልሰማ ከውጪ መጥቶ ያለምንም ጥያቄ ድብዳባውን ተቀላቀለ ፡፡ ከዱላው በተጨማሪ በጣም አጸያፌ ስድቦችን ሰደቡኝ፡፡ ብሄርህን የካድክ በብሄርህ የምታፍር ይሉኝም ነበር፡፡
– ከሚያዝያ 19-ሰኔ 26 2006 ባሉት ቀናት ለፍርድ ቤት አቤቱታ ማቅረብ አያድንህም በማለት አጸያፌ ቃላት በመሰንዘር ሰውነቴ ሊቋቋመው የማይችለው የአካል እንቅስቃሴ እንዳደርግ ተገድጃለሁ ፡፡
– በተለይ ግንቦት 11 ላይ የዞን9 አላማ ጠይቀውኝ ስናገር እውነቱን አውጣ በሚል በተደጋጋሚ ድብደባ የደረሰብኝ ሲሆን ደስታ እና ሃሰን የተባሉ ሽፋን ስሞች የሚጠቀመው መርማሪ በተደጋጋሚ ባደረሰብኝ ጥፌ ድብዳባ ጆሮዬ ተጎድቶ በህመም ላይ እገኛለሁ፡፡
– ቤቴ የተገኘው ማስታወሻ ደብተሬ ላይ ያሉትን ቃላት ነጣጥለው የሰጠሁት ቃል ውስጥ ያስገቡትን፣ ማስታወሻ ደብተሬ ላይ ያለው ሙሉው ነው አንጂ ተነጣጥሎ ቃሌ ውስጥ ተካቶ አልፈርምም በማለቴ አቶ ፈይሳ፣ አቶ ዬሃንስ ( ስማቸው የሽፋን አንደሆነ የምጠረጥረው) ታደሰ( ጥጋቡ በሚልም ይጠራል) ከፍተኛ ድብደባ አድርሰውብኛል፡፡
– ድብደባውም ጨለማ ክፍል ውስጥ በማስገባት አፌ ውስጥ ካልሲ በመወተፍ እግሮቼን ከላይ፣ ውስጥ እግሬን እና ከውስጥ ባቴን ታፋዬን እንዲሁም ጀርባዬን በእንጨትና በኮምፒውተር ገመድ ገርፈውኛል ፡፡
– የምርመራ ክፍሉ ወለል ላይ በደረቴ አንዲሁም በጀርባዬ እያገላበጡ በማስተኛት መላ ሰውነቴን ረግጠው ተራምደውብኛል፡። አፌን ሳይቀር ረግጠውታል፡። ይህንን በሚያደርጉበት ሰአት ሞራል የሚነካ ስድብ ይሳደቡ ነበር፡፡ ሁሉም የአካል ሆነ የስነልቦና ጥቃት ሲደርስብኝ እጄ በካቴና ታስሮ ሲሆን በቀን 15 ደቂቃ በላይ የጸሃይ ብርሃን የማላይበት ቀዝቃዛ ክፍል ውስጥ ለ76 ቀናት ቆይቻለሁ፡፡
*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

ማህሌት ፋንታሁን 
ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎቸ ስም ዝርዝር ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት እና የፌደራል ደህንነት መስሪያ ቤት አባላት መርማሪ ደስታ በዋናነት
ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – በተያዝኩባቸው ቀናት በሙሉ (በተለይ ሚያዝያ 18 በኋላ ባሉት የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት በሰፊው) 

የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ቢሮ ላይ
ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት

– በጠበቃ እና በቤተሰብ የመጎብኘት መብቴ ተጥሷል፡፡ ከተጎበኘሁም 10ደቂቃ ለማይሞላ ጊዜ በፓሊስ ተከብቤ ነበር፡፡

– በተደጋጋሚ በምርመራ ወቅት አመጽ ለማነሳሳት እነደጸፍሽ እመኚ እየተባልኩ በጥፊ እና በካልቶ ተደብድቤያለሁ፡፡

– በምርመራ ወቅት ልብሴን አስወልቀው አንድቀመጥ በማድረግ አይኔ ተሸፍኖ በምሽት ምርመራ ተደርጎብኛል፡፡

– ሙሉ ልብሴን እንዳወልቅ ተገድጄ ራቄቴን በወንድ መርማሪዎች ፊት ስፓርት አንድሰራ እገደድ ነበር ፡፡ “ሴትነትሽ አንዲህ ከሚዋረድ አመጽ እንዳነሳሳሽ እመኚ ተብያሁ”

– በሌሊት ግርፋት የሚፈጸምበት ክፍል ውስጥ ገብቼ ጫማሽን አውልቂ ተብዬ ጫማዬን አውልቄ ከቆምኩ በኋላ ውስጥ እግርሽን ከምትገረፊ አመጽ ማነሳሳትሽን አምነሽ ፈርሚ ተብያለሁ፡፡

– ሰጠሁት የተባለው ቃል ሰዎች በሚቀጥለው ክፍል እየተደበደቡ የጩኀት ድምጻቸው እየተሰማ ፈርሚ ተብዬ የተባልኩት ቦታ ላይ ሳላነብ በፍርሃት ፈርሜያለሁ።

– በተለያዬ ምርመራ ወቅቶች “ለነጭ አገሪትዋን የሸጥሽ ሸርሙጣ ውሻ ባንዳ…” አንዲሁም ለመጸፍ የሚከብዱ አፀያፈ ስድቦች በየቀኑ እሰደብ ነበር ፡፡

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

በፍቃዱ ሃይሉ

ስቃይና መብት ጥሰት ያደረሱብኝ ሰዎች ስም ዝርዝር ( ሁሉም የፌደራል ፓሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል አባላት) በተለይ 
-መርማሪ ታደሰ ወይም ጥጋቡ ( የሽፋን ስም ) 
– መርማሪ ጽጌ 
-መርማሪ ብቂላ
ዋና ዋና የማሰቃየት ተግባር የተፈጸመበት ቀንና ሰአት – ሚያዝያ 22 ( ከምሽቱ 2 ሰአት ገደማ)፣ ሚያዝያ 23 ከጠዋቱ 4 ሰአት፣ ግንቦት 6( ከምሽቱ 3 ሰአት ገደማ)፣ ሚያዝያ 24 ከጠዋቱ 4 ሰአት እና ከሚያዝያ 22 እስከ ግንቦት 6/2006 ድረስ ባሉት ቀናት ከእሁድ በስተቀር

የማሰቃየት ተግባራት የተፈጸመበት ቦታ – የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ህንጻ ላይ ቢሮ ቁጥር 35 ፣ 27 እና ቁጥሩን በማላስታውሰው የቃለ መጠይቅ ቦታ

ዋና ዋና ማሰቃየት ተግባራት
– ማአከላዊ ምርመራ በቆየሁባቸው ቀናት ከእሁድ በስተቀር ጠዋት ከሰአት ማታ እየተጠራሁ በዛቻ በአጸያፌ ስድብ ጭካኔ የተሞላበት ግርፌያ ጥፌና እርግጫ አንዲሁም ከአቅሜ በላይ የሆነ ስፓርት እየሰራሁ ቃሌን እንድሰጥ ተገድጃለሁ፡፡የተያዝክበትን ድብቅ አጀንዳ ንገረን በማለት ራሴን እንድወነጅል ተገድጃለሁ፡፡

– መርማሪው በመጀመሪያ ቀን ምርመራ በጥፌ መምታት የጀመረ ሲሆን እያንዳንዱን ጥያቄ ከጠየቀኝ በኋላ በጥፌ ይመታኝ ነበር፡፡ የዞን9 አላማ ጠይቆኝ ስነግረው ድብቁን አውጣ በማለት መሬት ላይ አንድቀመጥ እና ያደረኩትን ነጠላ ጫማ እነዳወልቅ አዞኝ በኮምፒውተር ገመድ እግሬን መግረፍ ጀመረ፡፡ በተጨማሪም በሆዴ አንድተኛ በማዘዝ እና እግሬን አጥፌ ከፍ አንዳደርገው በማድረግ ውስጥ እግሬን ገርፎኛል፡፡ ድብቄ አጀንዳህን ካልተናገርክ ነገ እዘለዝልሃለሁ በሚል አስፈራርቶኛል፡፡ ግርፌያው ውስጥ እግሬን ሲለበልበኝ ነበር ፡፡

– ድምጽ እንዲያፍን ሆኖ ወደተሰራው የስብሰባ አዳራሽ ተወስጄ በጥፌ እየደበደቡኝ የዞን አላማ ተናገር ተብዬ ተደብድቤያለሁ፡፡ ስቃዬ ሲበዛብኝም የፈጠራ ታሪክ አንዳወራ ተገድጃለሁ፡፡ እኔ የምጽፈው ኢትዬጲያ ውስጥ አብዬት ለማስነሳት ነው ብዬ እንድፈርምም አስገድደውኛል

– በምርመራ ወቅት እጄ በካቴና እነደታሰረ ለሰአታት ቁጭ ብድግ አንድል ተገድጃለሁ፡፡

– መርማሪው በአንድ ወቅት አራት የዞን9 አባላት ሆናችሁ ስለአላማው የተወያያችሁትን በቃል መስጫው ክስ ላይ ልጽፍ ነው ሲለኝ አንደዛ አይነት ውይይት ማድረጋችንን አላስታውስም ስለው እንዴት አታስታውስም ብሎ በጥፌ መማታት ጀመረ፡። በተደጋጋሚ ከመደብደብም በላይ እስክስታስታውስ እዚሁ ታድራታለህ በማለት ድብደባው በመቀጠሉ አስታውሳለሁ ብዬ ተገላገልኩ ፡፡ የሰጠሁት ቃል ላይም እንደፈለገው አድርጎ ጻፈው፡፡ እኔም በድብደባ ብዛት ፈርሜያለሁ፡፡

– ዞን9 ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት የሌለው ከሆነ ይህንን ህዝብ አንዴት ነው ነጻ የምታወጡት በሚል ሲጠይቁኝ የነጻ አውጪነት ሚና የለንም ስላቸው ከወንበሬ አንድነሳ አዘዙኝ፡። ከዚያም በቆምኩበት ግራ ብብቴን እና እጄን በአንድ እጁ አንዳልወድቅ ወጥሮ ይዞ በእግሩ ጭኔን በሃይል ደበደበኝ ፡፡ ከድብደባው በማስከተል ደግሞ እግሬ መሃል እግሩን በማስገባት ወደግራ እና ወደቀኝ በመምታት ተዘርጥጬ እንድቆይ በማድረግ እጄን ወደላይ አድርጌ እግሬ ግራና ቀኝ ተዘርጥጦ ( በተለምዶ ስፕሊት በሚባለው) በግራ እና ከቀኝ በመደብደብ እጄን ወደላይ አድርጌ እነድመረመር ተደርጌያለሁ፡፡ከዚህ ምርመራ በኋላ ለሁለት ቀን እያነከሰኩ ነበር፡፡

– በጥቅሉ ምርመራው በተከናወነባቸው ቀናት ከእሁድ በስተቀር ሳልደበደብ ቢያንስ በጥፌ ሳልመታ የቀረሁበት ቀን የለም፡፡ ድበደባዎቹ አብዛኛው ድብቅ አጀንዳችሁን ተናገር የሚሉ ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ በጣም ጥቃቅን በመሆኑ ምክንያቶች ነው ፡፡ መልስህ ንቀት አለበት ለምን አላስታወስክም በሚሉ ምክንያቶች ስደበደብ ነበር ፡፡

*ይህ ጽሁፍ ለኢትዬጲያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከገባው አቤቱታ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ከጎንዬሽ ጉዳዬች ውጪ ለ25ተኛ ጊዜ (በአጠቃላይ ለ27ተኛ ጊዜ) የተሰየመው ችሎት ዛሬም የደረጃ ምስክሮችን ሲያሰማ ውሏል፡። ከሳምነትት በፌት የተሰየመው ችሎት አቃቤ ህግ 41 ምስክሮች አሉኝ ነገር ግን ላገኛቸው ስላልቻልኩ ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤት ቆይተው ተጨማሪ ማፈላለጊያ ጊዜ ይሰጠኝ በማለት ጠይቆ ለዛሬ የተቀጠረ ቢሆንም ዛሬም “የሽብር ተግባሩ “ ዋና ምስክሮች ባለመገኘታቸው ፍተሻ ላይ ተገኝተናል ያሉ አምስት ምስክሮች ተሰምተዋል፡። የምስክሮቸን ቁጥርም 35 ነው በማለት ቀይሮታል፡፡
ባለፈው የተሰሙት 13 ምስክሮች ሲሆኑ በዛሬው ችሎት ባልተካደ ነገር ላይ ሲመሰክሩ የዋሉት የደረጃ ምስክሮች
14ተኛ ምስክር ተወዳጅ ኃ/ማርያም ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 34 ሲሆን የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ‹‹የመጣሁበት ኬዝ ግንቦት 7/2006 ዓ.ም በምኖርበት ልደታ 5ኛ አካባቢ የፌደራል ፖሊስ ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ጠይቆኝ በታዛቢነት ያየሁትን ለመመስከር ነው፡፡ ማህሌት ጤና ጥበቃ ሚ/ር ትሰራለች መሰለኝ፣ እዚያ መስሪያ ቤት ፖሊስ ማህሌት ኮምፒውተርና ጠረጴዛ ላይ ያለውን ሲበረብር አይቻለሁ፡፡ መንግስት መስሪያ ቤት የምትጠቀምበት ኮምፒውተር ላይ የተገኙ ሰነዶች ላይ ማህሌት ስትፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ የፈረምነው ግንቦት 7/2007 ዓ.ም ነበር፡፡ የገጹን ብዛት አሁን አላስታውስም፤ ወደ 40 ገጽ ይሆናል፡፡ እንግሊዝኛና አማርኛ ጽሁፎች አሉበት፡፡ የተወሰነ የፖለቲካ ይዘት የነበረው አለ፡፡ የፖለቲካ ፕሮግራም ማኒፌስቶ አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ ማህሌትን ሲጠይቃት ከኦነግ የወጣው የሌንጮ ፓርቲ ፕሮግራም ነው ብላለች፡፡ ጎስፕ ንግግሮችም አሉ›› ብሏል፡፡ ዳኛው ጎሲፕ በአማርኛ ምንድነው ሲላቸው ምስክሩ ‹‹ሽሙጥ ንግግር ነው›› ብለው መልሰዋል፡፡ ምስክሩ የተገኙ ሰነዶች ላይ ፌደራል ፖሊስ ሄደው እንደፈረሙና ይሄን ያደረጉትም ግንቦት 9/2006 ዓ.ም ነው ብለዋል፡
15ተኛ ምስክር ፀሐይ ብርሃኔ እድሜያቸው 33 የሆኑ የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ‹‹ግንቦት 7/2006 ዓ.ም ከቀኑ 4፡00 ፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ፖሊስ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አሳይቶ ቢሮ ሲፈተሽ ታዘብ ተብዬ ተገኝቼ ነበር፡፡ ሲ.ዲ እና ዲክሜንት ሲወሰድ አይቻለሁ፡፡ ከዚያ ፖሊስ በ9/2006 ዓ.ም ሄጄ በሶፍት ኮፒ የነበሩት ሰነዶች ፕሪንት ተደርገው ማህሌት የፈረመችባቸው ላይ ፈርሜያለሁ፡፡ በእንግሊዝኛና አማርኛ የተጻፉ ናቸው፡፡ በግምት ወደ 40 ገጽ ይሆናል፡፡ አብዛኛው የፖለቲካ ነክ ጽሑፎች ናቸው፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጽሑፎች አሉበት፡፡ ያየናቸው መረጃዎች ከእሷ ኮምፒውተር ላይ ስለመገኘታቸው አይተን ፈርመናል፡፡››
ለእኒህ ምስክር መስቀለኛ ጥያቄዎች ቀርበውላቸው ነበር፡፡
የጠበቆቹ መስቀለኛ ጥያቄ፡- ሲዲውን ማን እንዳመጣው
ታውቃለህ…ውስጡ ምን ነበረበት…
የምስክሩ መልስ፡- እኛ ራሳችን ቼክ አድርገናል፤ ባዶ ሲ.ዲ ነው፡፡
ጥያቄ፡- የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብለሃል….ስንት ናቸው
መልስ፡- አንድ ብቻ አይደሉም
ጥያቄ፡- የተለያዩ ፓርቲዎች ሰነዶች ብለዋል እኮ….እነዚህ ላይ ሁሉ ፈርመዋል
መልስ፡- አሁን በትክክል የማስታውሰው የሌንጮ ፓርቲ ሰነድ ላይ መፈረሜን ነው፡፡ ሌሎች ላይ አልፈረምኩም፡፡
(አንድ ሰነድ ቀርቦላቸው ፊርማው የእሳቸው ስለመሆኑ እንዲለዩ ተደርገው የእሳቸው መሆኑን አረጋግጠው የፈረሙበትን ሰነድ ይዘት ግን እንደማያውቁ አስረድተዋል፡፡)
ፍርድ ቤቱ ‹‹40 ገጽ ማየትህን ተናግረሃል፤ 40 ገጽ ላይ ፍርመሃል፣ ይዘቱንስ ታውቃለህ›› ብሎ ጠይቋቸው ምስክሩ ‹‹እያንዳንዱ ሰነድ ላይ ፍረሜያለሁ፤ ግን አላነበብኩትም፡፡ ክፍት የስራ ማስታወቂያ የሚል ግን አይቻለሁ›› ብለዋል፡፡ በተለየ የትኛውን ነው ያነበብከው ለተባሉት ደግሞ ‹‹አሁን አላስታውስም፤ የሌንጮ ሰነድ ላይ ፈርሜያለሁ፡፡ ማህሌት ፖሊስ ሲጠይቃት ሌንጮ የራሳቸውን አዲስ ፓርቲ እያቋቋሙ እንደሆነ ስትናገር ሰምቻለሁ›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
16ተኛ ምስክር ዳግማዊ እንዳለ 25 ዓመታቸው ሲሆን የመንግስት ሰራተኛና የአ.አ ከተማ የካ ክ/ከተማ ነዋሪ ናቸው፡፡ በ5ኛ ተከሳሽ አጥናፍ ላይ ለመመስከር እንደመጡ ተናግረው የአባቱን ስም አላስታውስም ብለዋል፡፡
“ሚያዝያ 17/2006 ዓ.ም 11፡00 ገደማ ከስራ ወደ ቤት ስሄድ 22 ትራፊክ ፖሊስ ጀርባ ፌደራል ፖሊስ የፍርድ ቤት ወረቀት አሳይቶ ታዛቢ ሁነኝ ብሎኝ ተገኝቻለሁ፡፡ አጥናፍ ቤት ገብተን ሰነዶች ሲገኙ አይቻለሁ፡፡ ፍላሽ፣ ሴኪዩሪቲ ኢን ኤ ቦክስ የሚል መጽሐፍ፣ ሲ.ዲ ተገኝተዋል፡፡ ሌሎች ታዛቢዎችም ነበሩ፡፡ ሰነዶቹ ላይ አጥናፍ ሲፈርም እኛም ፈርመናል፡፡›› ብለዋል፡፡
17ኛ ምስክር፡- ሳምሶን ሲሳይ ይባላሉ፤ 29 ዓመታቸው ሲሆን በግል ስራ ላይ የተሰማሩ ናቸው፡፡ አድራሻቸው አ.አ የካ ክ/ከተማ ነው፡፡ አጥናፍ ላይ ለመመስከር መምጣታቸውን ተናግረዋል ‹‹ሚያዝያ 17/2006 ዓ.ም 11፡00 አካባቢ ትራፊክ ጽ/ቤት ጀርባ ፖሊሶች ታዘብልን ስላሉኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ሲ.ዲ፣ ፍላሽ፣ የተለያዩ ዶክሜንቶች፣ ላፕቶፕ፣ ማስታወሻ ደብተሮች መገኘታቸውን አይቻለሁ፡፡ በዝርዝር አላስታውስም፡፡ ግን 150 አካባቢ መጽሐፍ ቆጥረናል፡፡ ፋክት መጽሔት ተገኝቷል፡፡ መጽሐፎቹ በእንግሊዝኛና አማርኛ የተጻፉ ናቸው፡፡ አጥናፍ የፈረመባቸው ላይ እኛም ፈርመናል፡፡›› ብለዋል፡፡
18ኛ ምስክር፡- እኒህ ምስክር ደግሞ በረከት ብርሃኔ የሚባሉ ሲሆን እድሜያው 29 ነው፡፡ በግል ስራ ላይ የተሰማሩና የአ.አ አራዳ ክ/ከተማ ነዋሪ ናቸው፡፡ 6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ላይ ለመመስከር እንደመጡ በመግለጽ ዘላለምን በአካል ለይተው አሳይተዋል፡፡ ‹‹ግንቦት 16/2006 ዓ.ም ማዕከላዊ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፖሊስ በጠየቀኝ መሰረት ታዝቤያለሁ፡፡ ሰነዶች ልናይ ስለሆነ እይልን አሉኝ፡፡ እሺ ብዬ ወደ ቢሮ ገባሁ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ይሆናል፡፡ እኛ ከገባን በኋላ ዘላለም ተጠርቶ መጣ፡፡ ላፕቶፑን ራሱ ፓስወርዱን ከፈተው፡፡ ከዚያ ከላፕቶፑ የወጡ ሰነዶች ፕሪንት ተደርገው ፈረምንባቸው፡፡ እንግሊዝኛም አማርኛም ነበር፡፡ ደሞ ምሳ ተጋብዘናል፡፡ ዘላለም ብላ ሲባል አልበላም አለ፡፡ አሁን ሰነዶቹ ምን እንደሆኑ አላውቅም፡፡ ዘላለም የፈረመበት ላይ ነው እኔ የፈረምኩት፡፡ ለማንበብ ግን ጊዜ አልነበረኝም፡፡ ስለዚህ ይዘቱን አላውቀውም፤ እሱ የፈረመበት ስለሆነ ብቻ ፈርሜያለሁ፡፡ አልፈርምም ያለው ሰነድ አልነበረም፡፡ ሌሎች ታዛቢዎችም ነበሩ፡፡ እነሱም ፈርመዋል›› ብለዋል፡፡
ምስክሮች ከመሰማታቸው አስቀድሞ አቃቤ ህግ ባለፈው የተሰጠው ቀጠሮ አጭር በመሆኑ ሌሎቹን ምሰክሮች ለማግኘት ረዘም ያለ ጊዜ ቀጠሮ አንዲሰጠው አንዲሁም አስመዝግቤያለው ካላቸው ሲዲዊች ውስጥ 7ቱ አንዲሰሙለት የጠየቀ ሲሆን የቀሩት ግን ሲዲውን የያዘው ባለሞያ ከአገር ውጪ በመሆኑ ማቅረብ አልቻልንም ብሏል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች ተከሳሾች ከታሰሩ አንድ አመት ሊሞላ ጥቂት አንደቀረ ምስክሮቸን ማዘጋጀት ቀደም ብሎ መሰራት የነበረበት የአቃቤ ህግ ስራ መሆኑን ነገር ግን በተደጋጋሚ እድል እየተሰጠው አንዳልተጠቀመበት በመጥቀስ ዛሬ የቀረቡት የሰው ምስክሮች መጨረሻ አንዲሆኑ እና የቀሩ ማስረጃዎቸን ለመስማት አጭር ቀጠሮ እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡ “ፍርድ ቤቱ” የአቃቤ ህግን ክርክር በመደገፍ የሚቀጥለውን ቀጠሮ ከአንድ ወር በላይ በማራዘም ግንቦት 18-21 2007 አም ድረስ እንዲሆን አንዲሁም የሲዲ ማስረጃዎቹ በወቅቱ ተሟልተው አንዲቀርቡና ቀሪ ምስክሮቹም በዚያው ቀን ወስኖ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡
የዞን9 ማስታወሻ
አንደሁልጊዜው ሁሉ የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ክስ ፓለቲካዊ ነው ያልተሰራ ወንጀል ምስክር አይገኝለትምና ፈጣን ፍትህን የማግኘት መብትን መቀለጃ ላደረገው ፍርድ ቤትም ሆነ የመንግስት ስራ አስፈጻሚ ጓደኞቻችንን ለመፍታት አሁንም ጊዜው አልረፈደም የሚለውን መልእክት ለማስተላለፍ አንወዳለን፡፡

በፍቃዱ ኃይሉ (ከቂሊንጦ እስር ቤት)
አስታውሳለሁ፣ከአራት ዓመታት በፊት የተሰራ አንድ የETV ‹ዘጋቢ ፊልም› ‹‹የግል ፕሬሱ መርዶ ነጋሪ ወይስ ልማት አብሳሪ?›› የሚል ርዕስ ተሰጥቶት ነበር፡፡ ‹ዘጋቢ ፊልሙ› የመንግስትን አቋም የሚያንፀባርቅ ስለነበር መንግስት መገናኛ ብዙኃን እንዲሆኑ የማይፈልገውንእና የሚፈልገውን በርዕሱ ቁልጭ አድርጎ ነግሮናል፡፡ እርግጥም ‹‹ልማት አብሳሪነት›› ውስጥ ምንም ስህተት የለም፤ ‹‹መርዶ ነጋሪ›› መሆንም የሚወደድ ነገር አይደለም (የሚቀር ባይሆንም)፡፡ ዛሬ ይህችን ደብዳቤ እንድጽፍላችሁ ያነሳሳኝ ‹‹ልማት አብሳሪነት›› በሚል ሥም ተለብጦ እየተሰራ ያለውን ስህተት (በጊዜ ማጣት) ካልተረዳችሁት ወይም ችላ ካላችሁት ቆም ብላችሁየምታስቡበት አፍታ ላውሳችሁ ብዬ በማሰብ ነው (ጊዜ አለኝና)፡፡
በመጀመሪያግን እንድትረዱልኝ የምፈልገው ነገር አለ፡፡ በስመ የEBC ጋዜጠኝነታችሁ የገዢው ፓርቲ ወገንተኛ ናችሁ የሚል ድምዳሜይዤ አልተነሳሁም፡፡ እንደዚያ ቢሆንማ ኖሮ ይህንን ደብዳቤ ልጽፍላችሁ አልወስንም ነበር፡፡ ይልቁንም፣ ወረድ ብዬ የምገልጸውን‹ስህተት› እየሰራችሁ ያላችሁት አንድም በጫና፣ አንድም በፍርሀት፣ አንድም ‹ትክክል› የሰራችሁ እየመሰላችሁ እንደሆነ በማመንነው ብዬ እገምታለሁ፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ዕድገት ገና ጨቅላ በሆነበት አገራችን ሙያችሁን የምታዳብሩበት ሌላ ሰፊ እና ሴፍ (Safe)ተቋም አጥታችሁም ሊሆን ይችላል፡፡ የስራ አጥነት በተጋነነበት የገዛ አገራችን ወር የሚያደርስ ምንዳ እና አበል የሚከፍል ሌላየሚዲያ ተቋም ማግኘት እንደሚቸግራችሁም አላጣሁትም፡፡ ነገር ግን ከነዚህ ሁሉ የሚበልጡትን ሙያዊ ስማችሁን (career) እናአገራዊ ኃላፊነታችሁን በነዚህ ሰበብ አስባቦች መጨፍለቃችሁን አልወደድኩምና የመናገር ኃላፊነቴን እነሆ!
‹‹ልማት አብሳሪ›› ወይስ ‹‹ይሁንታ አምራች››?
የዞን9 ጦማሪ እና የጋዜጠኝነት መምህሩ እንዳልካቸው ኃ/ሚካኤል ዞን 9 ላይ ባሰፈረው አንድ መጣጥፍ ‹የመንግስት ጋዜጠኞች› ‹‹ናችሁ›› የተባሉትን ‹‹ልማታዊ ጋዜጠኝነት›› እንዳልሆኑት ሲናገር የተጠቀመበት ቋንቋ ‹‹ይሁንታ አምራችነት›› የሚለውንነበር፡፡ ቋንቋው ለኔም ገላጭ ሆኖልኛል፡፡ በሕዝብ በጀት የሚተዳደሩ (የመንግስት) መገናኛ ብዙሃን በስመ ‹‹ልማታዊጋዜጠኝነት›› መንግስት ሊያሳካ የቻላቸውን ሥራዎች ብቻ ነቅሶ በማውጣት ማንቆለጳጰስ ‹‹ልማት አብሳሪነት›› ሊባል አይችልም፤ለገዢው ፓርቲ ሕዝባዊ ይሁንታን ማምረት እንጂ!
ነገሬንላብራራው፡፡ ድኅነትን ያልቀመሰ እና የሚወድ ኢትዮጵያዊ የለም፡፡ ድኃ የመሆንን ያህል የድኃ አገር ዜጋ መሆንም ያስጠላል፡፡አገራችን ከድኅነት ለመውጣት የምታደርገው መፍጨርጨር የመንግስት ጉዳይ ከሆነው በላይ የሕዝብ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከድኅነትመውጣት የሚቻለው ‹‹ልማት›› የሚለውን ቃል ደጋግሞ በመደስኮር አይደለም፡፡ እየተሰራ ያለውን ነገር መካድ ባይገባም እያልተሰራያለውን ነገር እና በስራው ስም እየጠፋ ያለውን ነገርም አብሮ መንቀስ እና ማጋላጥ ያስፈልጋል፡፡ እንደኔ፣ እንደኔ እውነተኛው‹‹ልማታዊ›› ይህንን አጋልጦ፣ ‹አውቆ በድፍረት ሳያውቅ በስህተት› በሁለቱም ሁኔታዎች የሚያጠፋውን መንግስታችንን ማረምየሚችል ሰው ነው፡፡ አሁን የEBC ጋዜጠኞች እያደረጋችሁ ያላችሁት ግን (ቀደም ብዬ በጠቀስኳቸው ሁኔታዎች ተገዳችሁ እንደሆነብጠረጥርም እንኳ) ‹‹ልማትን መደገፍ ማለት ገዢውን ፓርቲ መደገፍ ማለት ነው›› የማለት ያክል ነው፡፡ ልማታዊነት ሌላ በልማትሥም ለአምባገነኖች ይሁንታን ማምረት ሌላ፡፡
ከድኃሕዝብ መቀነት በተፈታ ወይም በሥሙ በተሰበሰበ ገንዘብ የሚተዳደረው እና ደመወዝ የሚከፍላችሁ EBC (ኢብኮ) እኔ ሞክሩትእያልኩ የምጨቀጭቃችሁን ዓይነት ጋዜጠኝነት እንድትሰሩ የማይፈቅድ መዋቅሮች እንዳሉት ሳልጠረጥር ቀርቼ  አይደለምይህንን ምክር የጻፍኩላችሁ፡፡ መዋቅሩንም ቢሆን መታገል፣ ችግሩን መነቅነቅ የሥራችሁ አካል ነው እያልኳችሁ ነው፡፡ በርግጥ፣እንዲህ አይነቱ እርምጃ የመረጣችሁትን safe መንገድ አደገኛ (risky) ያደርገዋል፡፡ ቢሆንም በመርሕ እና ሓቅእስከተመራችሁ ድረስ risk ውስጥ ደስ የሚል ነገር አለው (bitter sweet እንዲሉት ዓይነት) እያልኳችሁ ነው፡፡ሞክሩትና አትከስሩም፡፡
‹‹የእናንተ ገነት››፣ ‹‹የእኛ ገሀነም››
እናንተበልማቷ ወደር የላትም፣ ገነት ሆናለች እያላችሁ የምታወሩልንን ኢትዮጵያ ማን እንደምንላት ታውቃላችሁ? ‹‹እቲቪዮጵያ›› – የአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ጸሐፊ ቃልኪዳን ይበልጣል ነው ይህንን ሥም ያወጣላት፡፡ እውነቴን ነው የምላችሁ፡፡ በልማቷ ወደርያልተገኘላት፤ ከተማዋ የመብራትና የውኃ፣ ገጠሯ የማዳበሪያ እጥረት ያልገጠማት፤ መልካም አስተዳደር የሰፈነበት፣ ዴሞክራሲእንደፀበል የምንራጭባት ዓይነቷን ኢትዮጵያ እንኳን ኖሬባት መንገድ ላይ አይቻት አላውቅም፡፡ ትዝብቴን ግልጽ ለማድረግእንዲረዳኝ የዘንድሮውን የምርጫ ድራማ እና የኢብኮን አዘጋገብ ላጣቅስ፡፡
ግንቦትወር ላይ በሚካሄደው እና ብዙዎቻችን (አሸናፊውን ከወዲሁ እናውቀዋለንና) ‹‹የተበላ ዕቁብ›› እያልን የምንጠራውን ምርጫ2007 አስቡት፡፡ መንግስታችንን አስቡት፡፡ ምርጫ ቦርድን አስቡት፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎችን አስቧቸው፡፡ የኢብኮ ዘገባንአስቡት፡፡ ኢብኮ የኢሕአዴግ ተቀናቃኝ የሆኑትን ፓርቲዎች ደካማ ጎን የሚያብጠለጥልበት፤ የኢሕአዴግ -ግንባር አባላት የሆኑፓርቲዎችን ልደት ወይም አንዳች ሰበብ እየፈለገ የሚያቆለጳጵስበት፤ ምርጫ ቦርድ ሕገ-መንግስታዊ ግዴታውን ንቆ ወገንተኛየሆነበት (በነገራችን ላይ ‹‹ወገንተኛ የሆነበት›› የሚለውን ‹‹ለማን›› እንደሆነ ሳልጠቅስ ገና ገብቷችኋል እና ማስረጃማጣቀስ አያስፈልገኝም፡፡) ብሎም በዜናውም፣ በ ‹‹ዘጋቢ ፊልሞች››ም ሰበብ ለገዢው ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ የሚደረግበትዴሞክራሲያዊ ስርዓት – እውነት እንነጋገርና ምን ዓይነት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ነው?  እውነት የኢትዮጵያ ችግርየመሰረት ድንጋዮች በማስቀመጥ የሚፈታ ነውን? እውነት ኢብኮ የሚያቀርባቸው ሳምንታዊ ፌስቲቫሎች የሕዝብ ገንዘብ በከንቱከማባከን በላይ ፋይዳ አላቸውን?
እናንተ‹‹አሸወይና ነው›› እያላችሁ በእልልታ የምታቀርቡልን ዜና እኛ ‹‹እዬዬ›› የምንልበትን ጉዳይ መሆኑ ‹‹እናንተ››ን እና‹‹እኛ››ን የሁለት አገር ሰው እያስመሰለን ነው፡፡ እናንተ እና እኛ ግን እናንተም እኛን እኛም እናንተን መሆን የነበረብንየአንድ አገር መዳፍ ሁለት ጣቶች ነን፡፡ አንዳችን ጠፍተን አንዳችን  መትረፍ የማንችል መንትዬዎች፡፡ ኢትዮጵያችንኢትቪዮጵያን ብትመስልልን አንጠላም፡፡ የምንጠላው በሐሰት የተሸከመችው ስም ከብዷት እንዳትሰበር ነው፡፡
ይህንን ለናንት፣ ለEBC ጋዜጠኞች የጻፍኩትን ግልጽ ደብዳቤ እያነበበ እንዳለመብሰል (naivity) የሚቆጥርብኝ ሰው ጥቂት እንደማይሆንእገምታለሁ፡፡ በናንተ ጉዳይ naive ለመባል የደፈርኩት የEBCን ኩሸት በፍቅር የሚዋሹለት ‹‹ጋዜጠኞች›› ያሉትን ያክልመውጫው እንደመግቢያው አልሰፋ ብሏችሁ የቆያችሁም አላችሁ ብዬ በመገመቴ ነው፡፡ መውጫው ቀላል ነው፡፡ EBCን ከላይ እስከታችየውሸት ቋት ያደረገውን አሰራር በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መታገል፤ ከውስጡ፡፡ ዘላለም ለኢፍትሐዊነት ታዛዥ ሁኖ የውሸት ከመኖርአንድ ቀን የእውነት ጀግና ሁኖ መባረር – ቢያንስ አንድ ገጽ የሚወጣው የሕይወት ታሪክ ይወጣዋል፡፡
የዞን9 ማስታወሻ
ይህ ጽሁፍ በጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ተጽፎ በፍቱን መጽሄት ላይ የታተመ ሲሆን ለኢንተርኔት አንባብያን ይበቃ ዘንድ መልሰን አትመነዋል፡፡ 

በቀልድ የታጀበው ምስክሮችን የመስማት ውሎ -የዞን9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች ላይ
የኅሊና እስረኞቹ አጥናፍ፣ ማኅሌት፣ ዘላለም፣ በፍቃዱ፣ ናትናኤል፣ አቤል፣ ኤዶም፣ ተስፋለም እና አስማማው፡፡

ቀን አንድ (መጋቢት 21)

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆየው የማስረጃ መስማት ውሎ ዛሬ ምስክሮችን በማስማት ተጀምሯል፡፡ በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ ጉዳዬን ያስረዱልኛል ያላቸውን 17 ምስክሮች ያስመዘገበ ሲሆን 15ቱ በፍርድ ቤቱ ተገኝተው ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ አቃቤ ህግ ችሎቱ በዝግ ችሎት አንዲሆን የጠየቀ ሲሆን ምስክሮቼ እና የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለመጠበቅ ችሎቱ በዝግ ሊሆን ይገባል የሚለውን አቤቱታውን ጠበቆች በከፍተኛ ደረጃ ተቃውመውታል፡፡ ምስክሮቹ የጭብጥ ምስክሮች ሳይሆኑ ፍተሻን የታዘቡ የደረጃ ምስክሮች በመሆናቸው እና ስማቸውም በግልጽ ተከሳሾች ጋር ስለደረሰ ምንም አይነት የደህንነተ ስጋት የለባቸውም ከሚለው የጠበቆች ክርክር በኋላ ፍርድ ቤቱ በጉዳዬ ላይ ተወያይቶ ለመወሰን ረፍት ወስዷል፡፡ በዚህም መሰረት የአቃቤ ህግን አቤቱታ ውድቅ በማድረግ ችሎቱ በግልጽ ሆኖ መስክሮች ምስክርነታቸውን እነዲያሰሙ ታዟል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ምስክሮች አነማን ላይ አንደሚመሰክሩ እና ምን አንደሚመሰክሩ በተጠየቀው መሰረት ፍርድ ቤቱም በጠበቆቹ ስለተነሱት ነጥቦች የአቃቤ ህግን ምላሽ ጠይቋል፡፡ አቃቤ ህግም በዛሬው ዕለት የቀረቡት ምስክሮች በ2ኛ፣ በ3ኛ፣ በ5ኛ፣ በ6ኛ፣ በ7ኛ እና 8ኛ ተከሳሾች ( በስድስቱ የዞን9 ጦማርያን ላይ እና በጋዜጠኛ አስማማው ላይ ) ላይ እንደሚመሰክሩ ገልጾ የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቡድን በብርበራ ያገኛቸው ማስረጃዎች ከተከሳሾች የተገኙ ስለመሆናቸው ያስረዱልኛል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡
በምላሹም መሰረት የአቃቤ ህግ ምስክሮች ምስክርነታቸው ሰጥተዋል፡፡ ምስክርነታቸው ሲሰጡ በነበረበት ወቅት የተከሳሾችን ስም አለማወቅ አንዲሁም የተከሳሾችን መልክ አለመለየት የመሳሰሉት ጉዳዬች የተስተዋሉ ሲሆን ምስክርነታቸውን የሰጡት ሰዎች ስም ዝርዝር እና የምስክርነታቸው ጭብጥ በአጭሩ አንደሚከተለው ነው ፡፡
1.ሙሉጌታ መዝገቡ ለማ – ናዝሬት ነዋሪ ነኝ መአከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፓሊስ ታዛቢ ምስክር አንድሆን ጠይቆኝ በዚያ መሰረት ምስክር ሆኜ ተገኝቻለሁ፡፡ ከአቤል ከኮምፒውተሩ ላይ ጽሁፍ ሲወጣ እና ሲፈርም አይቼ እኔም ፈርሜያለሁ ፡፡ የጽሁፉን ይዘት አላነበብኩም አንዳንድ ቦታ አፍሪካ ሪቪው ኬንያ የሚል ቃል አይቻለሁ የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
2.በለጡ አበበ ዮሴፍ ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 32 ሲሆን ከፍተኛው ፍርድ ቤት የካ ምድብ ሰራተኛ ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ነዋሪ ሲሆኑ በማን ላይ ለመመስከር እንደመጡ ሲጠየቁ በስም እንደማያስታውሱት ገልጸው በአካል ግን ለይተው አሳይተዋል፡፡ መስካሪዋ በ6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ክብረት ላይ የሚመሰክሩ ሲሆን በተለየ ስም ሲጠሩት ተስተውለዋል
“የሽብርተኝነት ጉዳይ የሚያመለክት ይመስለኛል፡፡ ወደ 70 ገጽ አማርኛና 10 ገጽ እንግሊዝኛ ጽሁፍ ተገኝቷል፡፡ ያየሁትን አይቼ ፈርሜያለሁ፡፡” ካሉ በኋላ ተከሳሹስ ፈርሟል ተብለው ሲጠየቁ መጀመሪያ አላስታውስም ቢሉም እንደገና ሲጠየቁ ግን አዎ ፈርሟል ብለዋል፡፡
3.እታፈራሁ ጌታቸው ወልዴ የሚባሉ ሲሆን እድሜያቸው 36 ነው፡፡ በመንግስት ት/ቤት በአስተዳደር ሰራተኛነት የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ ማን ላይ እንደሚመሰክሩ ሲጠየቁ ፍቃዱ እና…..(ስሙ ጠፍቶባቸው ቆይተው) እ…አጥናፉ ብለዋል፡፡ በአካል ደግሞ በፍቃዱን አሳዩ ሲባሉ አጥናፍን አሳይተዋል፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ማእከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄደው ጽሁፎች ሲታተሙ ማየታቸውንና በፍቃዱ በፍቃደኛነት ሲፈርም ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለጽሁፎቹ ሲጠየቁ “የአማርኛ ጽሑፎች ናቸው፡፡ 60 ገጽ የሚሆን ‹ወያኔ ይውደም› ምናምን የሚል ጽሑፍ አይቻለሁ፡፡ እንግሊዝኛም አለው 10 ገጽ ይሆናል፡፡ በምስል ከውጭ ሰው ጋር ሆነው የሚነጋገሩትም አይቻለሁ፡፡ ይዘቱ ግን ግር ይለኛል፡፡” ብለዋል፡፡ አጥናፍን አስመልክቶ ደግሞ ‹‹የእሱንም በዚያው መልኩ ነው ያየነው፡፡ ዕለቱም ግንቦት 16/2006 ነው፡፡ ኮምፒውተሩ ላይ የነበሩትን ጽሁፎች እዚያ ለነበሩት ሲያሳይ ነበር፡፡ ጽሑፎችን አይቻቸዋለሁ….‹የጨለማው ቀን….የጨለማው ንጉስ› የሚል አይቻለሁ፡፡ ‹ኢትዮጵያ አንድ ናት› የሚልም አይቻለሁ፡፡ ወደ 30 ገጽ ይሆናል፡፡ ሁሉም ፕሪንት ተደርጎ ሁላችንም ፈርመንበታል፡፡››ብለዋል
ሶስቱ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ጠበቆች በሂደቱ ላይ አስተያየት አለን በማለት፣ ዶክመንቶቹ ፕብሊክ ዶክመንት ናቸው በአደባባይ የተጻፉ ጽሁፎቻቸው እና በማንኛውም ቦታ የሚገኙ ስለሆኑ ዶክመንቶቹን ክደን አልተከራከርንም የእኛ ክርክር ዶክመንቶቹ ለወንጀል ስራ የሚበቁ አይደሉም ነውና በዚህ ጭብጥ ዙሪያ ምስክር መስማቱ ያብቃልን የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡አቃቤ ህግ በበኩሉ ሁሉም ምስክሮች አንዲሰሙልኝ እፈልጋለሁ በማለቱ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ያስረዱልኛል ካለ ይቀጥል በማለቱ ምስክሮቹ ቀጥለዋል፡፡ ጠበቆች መስቀለኛ ጥያቄ ሳይጠይቁ ተከታዬቹ ምስክሮች መሰማታቸው ቀጥሏል፡፡
4.አራተኛው ምስክር አፈወርቅ ካሳ ይባላሉ፡፡ የግል ሰራተኛ ሲሆኑ እድሜያቸው 46 ነው፡፡‹‹ቀኑ ሚያዝያ 18/2006 ነው፡፡ የተከሳሹ አስማማው ቤት ጠዋት 3፡00 አካባቢ ሲፈተሸ ታዛቢ ነበርኩ፡፡ ጋዜጦች፣ መጽሔቶች፣ ፓስፖርት…ብዙ ወረቀቶች ላይ ‹‹አዎ የእኔ ናቸው›› እያለ ሲፈርም አይቻለሁ፡፡ እኔም ፈርሜያለሁ፡፡ ቤተሰቦቹም ቤት ውስጥ ነበሩ፡፡ አብዛኛው ያየሁት የግል መጽሄቶችን ነው፡፡ ማህተምም አይቻለሁ፡፡ ደሞ ቢሮው ሄደን ላፕቶፕ፣ ፍላሽ፣ ሲዲ፣ መጽሔቶች አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ የሚፈልገውን እየለየ ፈርመናል፡፡ ወደቢሮው የሄድነው በመኪና ነበር፡፡ ከዛ ደግሞ አድራሻችንን ይዘው ስለነበር ሰኔ 4….አይ 14/2006 ነው መሰለኝ ከማዕከላዊ ተጠርተን ላፕቶፕ ላይ የነበረውን ስዕሎችና የእንግሊዝኛ ንግግሮች ሲወጡ አይቻለሁ፡፡ የእኔ ነው ብሎ ሲፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡›› ብለው ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
5.አምስተኛ ምስክር አጌና አንከና ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 48 ሲሆን ነዋሪነታቸው አ.አ ነው፡፡ የሚመሰክሩት ደግሞ በ3ኛ ተከሳሽ ናትናኤል ላይ ነው፡፡ የምስክርነት ቃላቸው፣ ‹‹ሰኔ 17/2006 ለግል ጉዳይ ማዕከላዊ ነበርኩ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ፖሊስ ጠይቆኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ላፕቶፑ ላይ አማርኛ ጽሑፎች አይቻለሁ፡፡ ጽሑፎቹ የተከሳሹ ስለመሆናቸው አምኖ ሲፈርምባቸው ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ ይዘቱን ግን አላነበብኩትም፤ አልተረዳሁትም፡፡ የገጹን ብዛትም አላስታውስም፡፡›› የሚል የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
6.ስድስተኛ ምስክር ገብረጨርቆስ ገብረመስቀል ይባላሉ፡፡ የ50 ዓመት የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ ምስክሩ በአስማማው ላይ ለመመስከር እንደመጡ ቢናገሩም በአካል ግን ለይተው አላወቁትም፡፡ እንዲያውም አስማማውን አሳዩ ሲባሉ አቤልን አሳይተዋል፡፡
ከፍርድ ቤቱ ውሎ በኋላ አስተያየታቸው የሰጡት የተከሳሾች ጠበቆች አቃቤ ሀግ ያቀረባቸው ምስክሮች ወረቀት ሲፈረም አየን ከማለት ውጪ ምንም አይነት ለሂደቱ ቁም ነገር ያለው ምስክርነት የሚሰጡ አይደሉም ፡፡ ተከሳሾች ተገኘባቸው የተባለው ጽሁፍ የአደባባይ ዶክመንት ከመሆኑም በላይ አልተገኘብንም ብለን ክደን አልተከራከርንም በይዘቱ ላይ ክርክር ስላልተደረገ መስቀለኛ ጥያቄ ለማቅረብም ብዙ አልጨነቅንም ብለዋል፡፡አቃቤ ሀግ የወንጀሉን የመጀመሪያ ደረጃ ጭብጥ የሚያሳዬ ምስክሮችን ያቅርብ አይቅርብ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የማስረጃ ማሰማት ሂደቱ ነገ ይቀጥላል፡፡
ቀን ሁለት (መጋቢት 22)

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡

ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ የተሰሙት ምስክሮች
7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡
8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡
9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡
10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)
11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡
12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡
በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡
ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡


የዞን9 ማስታወሻ
አቃቤ ህግ የሌሉትን ምስክሮች ፍለጋ በማለት ለሚያባክነው ጊዜ ፍርድ ቤቱ አንደተለመደው ተባባሪ መሆኑ የፍትህ ስርአቱን በአጠቃላይ እና ይህንን መዝገብ ሂደት ይበልጥ አሳፋሪ አድርጎታል፡፡ አሁንም ቢሆን የተከሳሾች አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብት ተጠብቆ ሁሉም ተከሳሾች ነጻ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ እንዲሰናበቱ አጥብቀን እንጠይቃለን ፡፡
ያልተሰራ ወንጀል ምስክር አይገኝለትም ፡፡

ዞን9

የዞን ዘጠኞች እና የጋዜጠኞቹን ጠቅላላ የእስካሁኑን የፍርድ ሂደት በእንግሊዘኛ በ Trial Tracker Blog ላይ ያገኙታል፡፡