ጎንደሬው የጃማይካ ሰው
ዶ/ር በርናንድ ብራድሊ አንደርሰን ልደቱ ቅድስት ካትሪን ደብር ጀማይካ ዉስጥ ነዉ፡፡ ወሩ መስከረም፣ ቀኑ 21፣ ዓመተ ምሕረቱ 1944፣ አቆጣጠሩ በአዉሮጳውያን፡፡ ቅድስት ካትሪን አጥቢያ ከእርሻዉ መካከል ነበር ያደገዉ፡፡ ዕድሜዉ ለትምህርት ሲደርስ ካሪቢያን ዉስጥ አንጋፋ ከሚባለዉና ከተከበረዉ ዎልማር የወንዶች ትምህርት ቤት ገባ፡፡ ወደ አሜሪካ ምድር የዘለቀው በ1960ዎቹ ሲሆን በዋሽንግተን ዲሲ ዝነኛዉ ሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ በከፍተኛ ማዕረግ የመጀመሪያዉን የባችለር ዲግሪ አገኘ፡፡ ከክፍሉ ቀዳሚ ሆኖም ወደ ሕክምናዉ የትምህርት ዘርፍ ተሻገረ፡፡ ቀን ቀን ትምህርቱን እየተከታተለ፤ ሌሊቱን እየሠራና ራሱን እየረዳ ትምህርቱን ቀጠለ፡፡
እ.ኤ.አ በ1970ዎቹ የመጀመሪያ ዓመታት ላይ በቀዶ ጥገና ሕክምና በከፍተኛ መዓርግ ተመረቀ፡፡ በትምህርትና በሥራ የበለጸገዉና ገና በለጋነቱ በትጋቱ የታወቀዉ፣ የቅርብ ጓደኞቹ በርኒ የሚሉት በርናንድ፤ የሕክምና ትምህርቱን ጨርሶ እንደተመረቀ ወደ ትዉልድ ሀገሩ ጃማይካ ተመልሶ በኪንግስተን የሕዝብ ሆስፒታል ማገልገል ጀመረ፡፡ ኪንግስተን የሕዝብ ሆስፒታል ነጻ ሕክምና የሚሰጥበት፣ ለተቸገሩና ዐቅም ለሌላቸዉ የሚለገስበት በመሆኑ ቀልቡን ገዛዉ፡፡ ወትሮም የሕክምና ሙያ ለአምሳያ ፍጡር የመድረስ መንፈስ አለዉና ከዶ/ር በርናንድ አንደርሰን ዉስጣዊ ተፈጥሮና ተልዕኮ ጋር ገጠመ፡፡ ዶ/ር አንደርሰን ሕሙማንን ከማከም በላይ ተተኪ ወጣቶችን ማስተማርና ማዘጋጀትን እንደ ቃል ኪዳኑ ነበር የሚያየዉ፡፡
እዚያም ጀማይካ ከሕክምናዉ ጎን ለጎን መምህር ሆኖ ብዙዎችን አሠልጥኗል፡፡ ዶ/ር በርናንድ የጃማይካ የሆስፒታል ተልዕኮዉን እንዳገባደደ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ ተመለሰ፡፡ ነገር ግን ሀብትና ዕድሉ ወዳላቸዉ – ትርፍና ገንዘብ ወደሚጋበስባቸው ሆስፒታሎች ዓይኑን አላነሣም፡፡ እንዲያዉም የጤና ከለላና ሽፋን የሌላቸዉን ለመድረስ የሚችልበትን የቀድሞዉን ዲሲ ጄኔራል ሆስፒታል ነዉ የተቀላቀለዉ፡፡ ልዩ ተሰጥዖና ክህሎት ያለዉ ዶ/ር በርናንድ የሥራዉን ብቃትና የአመራር ችሎታዉን በዚያ ሆስፒታል ለማስመስከር ጊዜ አልወሰደበትም፡፡
በዲሲ ጄኔራል ሆስፒታል በሊቀ መንበርነትና የቀዶ ጥገና ዳይሬክተር በመሆን ሆስፒታሉ በሀገሪቱ ‹ዕዉቅና ያገኘ ሆስፒታል› ተብሎ እንዲጠቀስ ያደረገ ባለሙያ ነበር፡፡ ሲሠራ ውሎ ቢያድር ደከመኝ የማይል፣ ‹ሕሙማንን ማከም ተልዕኮዬ ነው› ብሎ የሚያምን ሰው ነበር፡፡ ዶ/ር በርናንድ አንደርሰን መኖሪያዉን በመሠረተባት የአሜሪካ ርዕሰ መዲና ዲሲ፣ በሮድ አይላንድ መንገድ ላይ የግል የሕክምና ክሊኒክ መሥርቶ በመደበኛዉ ሥራዉ ላይ አከለበት፡፡ ዶ/ር በርናንድ ክሊኒኩን ሀብት በበዛበት መንደር ሳይሆን የችግረኞቹን ቀየ ፈልጎና ይሁነኝ ብሎ ነበር ያቋቋመዉ፡፡ የመክፈል ዐቅም የሌላቸዉ ሕሙማንን በዚያ ክሊኒኩ በራሱ ወጪ ሕክምና መስጠቱን ዛሬ ድረስ በምስጋና የሚያነሡት ብዙዎች ናቸዉ፡፡
ዶ/ር አንደርሰን ስሙ ሳይጠቀስ፣ ለታይታም ሳይደርስ፣ ለተማረበት ትምህርት ቤት የአንድ መቶ ሺህ ዶላር ስጦታ የቸረ ለጋስ ሰው ነዉ፡፡ ይህ እንዲያውም ለአብነት ያህል ተነሣ እንጂ ዶ/ር አንደርሰን ‹ቀኝህ ሲሰጥ ግራህ አይመልከት› የሚለውን በተግባር ያሳየ፣ ልዩ ጸጋ የተጎናጸፈ ሰዉ ነበር፡፡ ዶክተር በርናንድ አንደርሰን ሕሙማንን መከባከብና ማከም፣ ችግራቸዉን ተቸግሮ፣ ቋንቋቸዉን ተናግሮ አምላክ የሰጠዉን ችሎታና በሰዉኛ የሚችለዉን ማድረግ የሕይወት ተልዕኮዉ ያደረገዉ ገና አንድ ፍሬ ወጣት እያለ ነዉ፡፡
አንድ ቀን ከሰዉ ዘር መፍለቂያዋ ከጥቁር ሕዝብ መኩሪያ ሀገር ኢትዮጵያ፤ እነ ማርክስ ጋርቬ “ወደ ራሳችን እንመለስ” ወዳሉባት ጥንታዊት ምድር ሄዶ የማገልገል ሕልም ነበረው፡፡ ያ ሕልሙና ራእዩ ይሳካ ዘንድ የኑሮ አጣማጁ ሲስተር እማዋይሽ ምክንያት ሆነችና ከምድረ አሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ለመጓዝ ሐሳብ ፀነሰ፡፡
ስለ ኢትዮጵያ ማንበብ፣ ስለ ኢትዮጵያ መመራመር ይወድ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ስም በተጠራበት ቦታ ሁሉ መገኘት አይሰለቸውም ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ይመሰጣል፡፡ ለሌሎች ወገኖቹ መንገርና ስለ ኢትዮጵያ እንዲያውቁ መጎትጎት ይወዳል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ማጥናት፣ ቤተ ክርስቲያን መሄድና ከአባቶች ጋር መወያያት ያስደስተው ነበር፡፡ የትዳር ጓደኛው ሲስተር እማዋይሽ ደግሞ ይኼ ደግ ሰው ኢትዮጵያ መጥቶ ይህንን የተከፈተ ልቡን ለሀገሯ ሰው ቢያስረክበው፣ ደግነቱን ቢያርከፈክፈው ትመኝ ነበር፡፤ መመኘትም ብቻ ሳይሆን ትጎተጉትም ነበር፡፡
‹‹ብዙ ጊዜ ሀገሬ ኢትዮጵያ ገብተን እንድንሠራ እነግረው ነበር፡፡ እርሱም በዚህ ላይ አስቦ እንደሚወስን ይገልጥልኛል፡፡ ከብዙ ጊዜ በኋላ አንድ ማለዳ ‹ላንቺ አስደናቂ ዜና አለኝ› አለኝ፡፡ በጉጉት ጠበቅኩ፡፡ ‹ላንቺ ስል ወደ ኢትዮጵያ ልሄድ ወሰንኩ› አለኝ፡፡›› ትላለቺ ሲሰተር እማዋይሽ ያንን ቀን ስታስታውሰው፡፡
እርሱም አንድ አስቀደመና ታንዛኒያን፤ ኬኒያን ሄዶ ጎበኘ፡፡ አፍሪቃ የምትቃትትበትን፣ ጫንቃዋን የያዛት የትላንቱ የቅኝ ዛር እንዳልለቀቃት አይቶ አዘነ፡፡ አስከትሎም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣ የድህነቱና የችግሩን መክፋት ተመለከተ፡፡ ነገር ግን አዘነ እንጂ ሸሽቶ አልተመለሰም፡፡ ከአዉሮፕላኑ ሲወርድ አየሩን ሲምገዉ – ሕልሙን አስታወሰዉ፡፡ የሕክምና ተቋማቱን ሲጎበኝ ሕሙማኑ ተኮልኩለዉ ቢመለከት ልቡ ተሰበረ፡፡ አዲስ አበባ ታላላቆቹ የግልና የመንግሥት የሕክምና ተቋማት ከእነርሱ ጋር እንዲሠራ ለመኑት፡፡ እርሱ ግን ወደ ገጠሩ መቅረብ ወደ ድኻው መጠጋት ይወድ ነበርና ከተሜዉን ጎብኝቶ ወደ ገጠሮቹ ሊመለከት አዘገመ፡፡ የሐኪም እጅ ማየት ቀርቶ መልኩና ገጹ የናፈቃቸዉ ወገኖች አጋጠሙት፡፡ በርካታ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጠዉ መጥተዉ ከየሆስፒታሉ ደጃፍ ተኮልኩለዉ አምላካቸዉን እየተማጠኑ፤ ከዕለታት አንድ ቀን የሐኪም እጅ እንዲነካቸዉ ሳምንታትን የሚጠብቁ ምስኪኖች ልቡን ነኩት፡፡ መንፈሱን ሳቡት፡፡ ጎንደርም በፍቅሯ ነደፈቺዉ፡፡ ቅርልኝ አለቺዉ፡፡ ዕድሜዉ ከግማሽ ምእተ ዓመት በላይ ለሆነዉ ለጎንደር ሆስፒታልና የሕክምና ኮሌጅ እጁን ሰጠ፡፡ ዶ/ር በርናንድ አንደርሰን የዋሽንግተን ዲሲዉን ስመ ጥር ሐኪም የጎንደር እጆች አቀፉት፡፡ ፋታና ዕረፍት አላስፈለገውም፡፡ ወትሮም ዕረፍቱ፣ ቀድሞም ምቾቱ ለሕሙማን መድረስ – ለተቸገረ ዋስ መሆን ነበረ፡፡ የቀናት ስምና ቁጥር ለዶ/ር በርናንድ ዋጋ አልነበራቸዉም፡፡ ከአጸደ ሥጋ እስከተለየበት ጊዜ ድረስ ለእርሱ ቀናት ማለት የሥራና ሰዉን የማገልገያ ጊዜያት ናቸዉ፡፡
ዶ/ር በርናንድ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የቀዶ ጥገና ትምህርት ክፍልን የተቀላቀለው በ1997 ዓም ነበር፡፡ ዶ/ር በርናንድ በኮሌጁና በሆስፒታሉ በነበረዉ ቆይታ የቅድመ እና ድኅረ ምረቃ ተማሪዎችን ከማስተማር ጎን ለጎን በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል ሕሙማንን በማከም ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድርጓል፡፡ በተለይም የቀዶ ጥገና ሕክምና ትምህርት ክፍል ሥርዓተ ትምህርት በየጊዜዉ እንዲሻሻል የነበረዉ የላቀ ሚና ምንጊዜም በትምህርት ክፍሉ አባላት ኅሊና የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ዶ/ር በርናንድ ዕዉቅ ቀዶ ጥገና ሕክምና ባለሞያ እንደመሆኑ ያለዉን እጅግ ሰፊ ዕዉቀት፣ ክህሎትና ልምድ ለተማሪዎቹና ለሞያው ሰዎች በማካፈል በርካቶች በሞያዉ የተካኑ እንዲሆኑ ያለማሰለስ ሠርቷል፡፡ በተለይም የሆስፒታሉ የቀዶ ሕክምና ባለሞያዎች ብቻቸዉን ሊሠሯቸዉ የሚቸገሩ የጉበት ካንሰር፣ የጣፊያ ካንሰር፣ የልብና የደም ሥር፣ የመሳሰሉትን ቀዶ ጥገናዎች በማከናወን ሌሎቹ ልምድ እንዲቀስሙ ማድረጉ ለሞያዉ መጎልበት ከነበረዉ ከፍተኛ አስተዋጽዖ በተጨማሪ ሕሙማኑ ፈዉስ እንዲያገኙ ያደረገዉ ተኪ የለሽ ተግባር ከፈጣሪ የተላከ እስከመባል ያደረሰው ነበር፡፡
በበርናንድ ዘንድ ሥራ ሲያልቅ እንጂ ሰዓት ሲያልቅ ማቆም አይታሰብም፡፡ አንድ ቀን እንዲህ ሆነ፡፡ እርሱና ተማሪዎቹ ከጠዋት እስከ ማታ ቀዶ ጥገና ሲያደርጉ ዋሉ፡፡ ምሳ አልነበራቸውም፡፡ ልክ ፀሐይዋ ማቆልቆል ስትጀምር ጨረሱ፡፡ ጨርሰው ልብሳቸውን ሲያወልቁ ግን አንድ የገጠር ሰው አንኳኩ፡፡ ‹ወረፋ እየጠበቅኩ ነበር›› አሉ ረዳት ሐኪሙን፡፡ ‹‹አባቴ አሁንማ መሸ ነገ ይምጡ›› አላቸው፡፡ አማራጭ አልነበራቸውምና ከዘራቸውን አንሥተው ጉዞ ጀመሩ፡፡ በርናርድ ድምጽ ሰምቶ ወጣ፡፡ ረዳቱን ጠየቀው፡፡ ረዳቱም ያደረገውን ነገረው፡፡ በርናርድ አዘነ፡፡ ‹‹እንዲህ ነበር ያስተማርኩህ›› አለው ረዳቱን፡፡ ‹‹በል ቶሎ ተከትለህ ጥራቸው›› ሲል አዘዘ፡፡ ሰውየው ተጠሩና እንደገና ልብስ ተለብሶ ቀዶ ጥገናው ቀጠለ፡፡ ይኼ ረዳት ሐኪም ዛሬ ታዋቂ የቀዶ ጥገና ሐኪም ሆኖ እንዲህ አለ ‹‹ያንን ትምህርት ስላስተማረኝ ተመርቄ ሰው የማይደርስበት ገጠር ገባሁ››፡፡
በርናርድ በሀገራችን በብቸኝነት የጉበት ካንሰርና ተዛማጅ በሸታዎች ቀዶ ሕክምና በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል እንዲሰጥ ያደረገ የሞያ ቁንጮ የነበረ ታላቅ ሰዉ መሆናኑን መመስከር አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን እጅግ በጣም ተገቢም ነዉ፡፡
“እስመ በትኅትና ይትረከብ ልዕልና” እንዲል የሕክምናዉ ሊቅ እኔን እዩኝ ሳይል፣ አለሁ ብሎ ሳይፎክር፣ ዕወቁኝ ብሎ ሳያዉጅ፣ ካልተወለደበት ወገን መካከል አገለገለ፡፡ እንደ ሀገሬዉ ባሕል እጅ ነሥቶ ፣ በባላገሩ ምርቃት ተመርቆ፣ ለድኾችና ረዳት ለሌላቸው ዋርካና መጠጊያ ሆነላቸዉ፡፡ በፍቱን እጁ ዳበሳቸዉ፡፡ ለወትሮው አመሰገኑት፡፡ በሄደበት በተገኘበት ቤት ያፈራዉን ሰንቀዉ እያመጡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ አሉት፡፡ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ፡፡ አንዲት ምስኪን እናት መጡ፡፡ እርሱም አከማቸው፡፡ ድህነታቸው ማግኘት ያለባቸውን ሕክምና አልከለከላቸውም፡፡ ከቅኖች ጋር አምላክ ይሠራልና ሴትዮዋ በበርናርድ ታክመው ዳኑ፡፡ ከቀናት በኋላ ሊያመሰግኑት ወደ ሆስፒታሉ ተመለሱ፡፡ መርቀው መርቀው ጨረሱና ከጉንፋቸው እጃቸውን ሰድደው አንድ ነገር አወጡ፡፡ ዐሥር ብር፡፡ ‹‹ሌላ ምንም የለኝም፤ በዚህ ግን ምሳ ብላበት›› ብለው ሰጡት፡፡ ሰው አክባሪው በርናርድ ዐሥር ብሩን አመስግኖ ተቀበለና የዐሥር ብር ምግብ ወደሚሸጥበት ቦታ ሄዶ ምሳ በላላቸው፡፡
ለዚህ ነበር ድፍን ጎንደሬ እያለቀሰ የሸኘው፡፡ አንድ አልቃሽ ያወረደችው ሙሾ የጎንደርን ስሜት ሳይገልጠው አይቀርም
የማን ዘመድ ሞተ አትበለኝ ሀገሬ
ጎንደር ሰው ሞቷታል እናላቅሳት ዛሬ
በርናርድን የጎንደር ሰው የሚያውቀው የተሸከመ ሰው ሲያይ ሸክሙን ተቀብሎ፣ በመኪናው ጭኖ ቤቱ ሲያደርስ፤ የተጎዳ ሰው ሲያይ ከመኪናው ወርዶ ችግሩን ሲጋራ፤ ወደ ሕክምና ያልመጣ ሰው መንገድ ላይ ሲያገኝ አባብሎ አምጥቶ ሲያክም ነው፡፡ ከየሕክምናዉ ተቋም ተኮልኩለዉ የሚያያቸዉ ሕሙማን ቢያሳዝኑት – መጠለያ ለማሠራት ወጠነ፡፡ ሀገር አቆራርጠዉ ለሕክምና የሚመጡትን ለመታደግም ሆስፒታል አስገነባ፡፡ በአዞዞ በዶ/ር በርናንድና በባለቤቱ የተገነባዉ ይህ ሆስፒታልም ለአንድ መቶ ሕሙማን ማረፊያ መኝታ እንዲኖረዉ ተደርጎ የተገነባ ነዉ፡፡ ምንም እንኳን የሆስፒታሉን ሥራ ጀምሮ ለማየት ዶ/ር በርናንድ በሥጋ ቢለይም ስሙን የተከለበትን ራእይ ትውልዱ ያየዋል፡፡ አደራዉንም ይሰማዋል፡፡
ዶ/ር በርናንድ አንደርሰን የሕክምና ሊቅ ብቻ አልነበረም፡፡ ዘርፈ ብዙ ተሰጥዖም ነበረዉ፡፡ በሥነ ሕክምናዉ በጣፊያና በጉበት ሕመም ለሚሰቃዩ በልዩ ጥበብ ብልቶቹ የሚሠሩበትን ዘዴ በምስል ነድፎ የባለቤትነት (ፓተንት) ያለዉ ባለሞያ ነበር፡፡ ዛሬ መዝገብ የያዛቸዉ በዓለም አቀፍ ደረጃ የባለቤትነት ዕዉቅና የያዘባቸዉ ሁለት መሣሪያዎች አሉት፡፡ የግጥም ስብስብ መጽሐፉ ርዕስ Limbic glimpses ይሰኛል፡፡ ዲዛይን በማድረግም ልዩ ችሎታ ነበረዉ፡፡ ዛሬ በአዞዞ የቆመዉ ሆስፒታሉም የ ዶ/ር አንደርሰን ዉጥን ነዉ፡፡ አንዲትም ዕለት ቸል ብሎ ችግርን ለማለፍ የማይፈቅድ፣ ፊት ለፊት ገጥሞ ተፈጥሮን ለመግራት ሲሞክርና ሲለፋ የቆየ፤ ሙሉ ዕድሜዉን በጥድፊያ ሲሠራበት የኖረ ታላቅ ሰብእና ነበረው፡፡
ዶ/ር አንደርሰን ኢትዮጵያን ዐዉቋት ነዉ የወደዳት፡፡ መንፈሳዊ ሕይወቱንም ከጥንታዊዉ እምነቷ ጋር አዋሕዶት ነበር፡፡ ጊዜ ሲያገኝ ወደ ቁስቋም ማርያምና ወደ ደብረ ብርሃን ሥላሴ መሄድ ያስደስተው ነበር፡፡ የክርስትና ስሙ ገብረ ሥላሴ ሲሆን የንስሐ አባትም ነበረው፡፡ ደግሞ እንደ ቅዳሴ የሚወደው ነገር አልነበረም፡፡ ገና በሕይወት እያለ በዚያ በተራራ ላይ እቴጌ ምንትዋብ በተከሏት በደብረ ፀሐይ ቁስቋም ማርያም ለመቀበር ምኞቱን ገልጦ ነበር፡፡ ‹ዛቲ ይእቲ ምዕራፍየ ለዓለም› ብሎ፡፡ በሕመም ተይዞ በአሜሪካን ሀገር እያለ፣ ከዚህ ዓለም ሊሰናበት ሲደርስ ባለቤቱን ‹‹ወጭዉ የማይበዛብሺ፣ አንቺንም የማያደክምሽ ከሆነ ኢትዮጵያ፣ ጎንደር ቁስቋም ብቀበር እወድ ነበር›› ብሎ ተናገረ፡፡ ይህንንም ብሎ ታኅሣሥ 23 ቀን 2007 ዓም ሁለት ልጆቹን ትቶ ዐረፈ፡፡
ሲሰተር እማዋይሽና ወዳጅ ዘመዶቹም ቃሉን አክብረው አስከሬኑን ወደ ጎንደር አመጡት፡፡ የዐርባ አራቱ ታቦት ካህናት አንድ ሆነው ወጥተው፣ ድፍን የጎንደር ሕዝብ ከአድያም ሰገድ ኢያሱ ወዲህ አልቅሶት በማያውቅ ልቅሶ ወደ ቁስቋም ሸኘው፡፡ ታሪኩ፣ ሥራዉና ውለታዉ ግን የብዙዎች ቤት ውስጥ ገብቷልና ይኖራል፡፡ ‹ለዓለም ይሄሉ› እንዲል፡፡



