ጠላ፣ ጥብስና ግድብ

ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ሲመኙት የኖረ፣ የትውልድን ሕልም እውን ያደረገ፣ በዘመናዊ ታሪካችን ውስጥ ሊጠቀስ የሚችል የዚህ ትውልድ ሥራ ነው፡፡ ‹ዓባይን መገደብ› ታላቅ ሐሳብ፣ ታላቅም ውሳኔ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከአካባቢው ሀገራት ጋር የምታደርገውን ውይይት ቋንቋውን የቀየረ፣ የግዮን ምንጩ ከኢትዮጵያ ተራሮች መሆኑን ከብራና አውርዶ መሬት ላይ የጻፈ ነው፡፡ 
 
ስለ ሕዳሴው ግድብ የሚሠሩት ማስታወቂያዎች ግን ፈጽሞ ግድቡን የማይመጥኑ፣ እንኳን ለዓባይ ግድብ ለኛ ቤት አጥርም የማይሆኑ፣ በውስጣቸው ምንም ዓይነት ሀገራዊ ርእይና ፍልስፍና የሌለባቸው፤ ከጠላና እንጀራ የማያልፉ ናቸው፡፡ እንዴው ግድቡ አፍ ስለሌለው እንጂ በስም ማጥፋትና በክብረ ነክ ወንጀል ይከስ ነበር፡፡  የታሪክ ባለሞያዎች፣ የፖለቲካ ጠበብት፣ የኪነ ጥበብ ልሂቃን፣ የእምነትና የባሕል ምሁራን፣ የሥነ ቃል አጥኒዎች፣ የሐሳብ መሪዎችና የሕዳሴ ኮከቦች መነጋገሪያ፣ መከራከሪያ፣ ሐሳብ ማራቀቂያ፣ ትውልድ መቅረጫ፣ ትውልድ ማነሣሻ፣ መሆን የነበረበት የሕዳሴው ግድብ የቀልደኞች ማቧለቻ ሲሆን እንደማየት ያለ የክፍለ ዘመኑ ርግማን የለም፡፡

እኔ እንዲያውም እነዚህ ግድቡን የማይመጥኑ ማስታወቂያዎች በግብጽ ነው እንዴ ስፖንሰር የሚደረጉት? እላለሁ፡፡ ግድቡኮ የግንባታ ሂደት ጉዳይ ነው፡፡ መንግሥት ከአንድ ኮንትራክተር ጋር ተነጋግሮ የሚያጠናቅቀው፡፡ ዋናው ጉዳይ አስተሳሰቡ ነው፡፡ ለምን እንገነባዋለን? የምን ማሳያ ነው? ዓባይን እንገድባለን ስንል ምን ማለታችን ነው? ዓባይ በኢትዮጵያ እምነት፣ ታሪክ፣ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ባሕል ውስጥ ምን ቦታ ነበረው? አሁን ወደየትኛው ቦታ እየወሰድነው ነው? ዓባይን የመገደብ ሂደትና ስኬት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ መፍጠሪያ መስፈንጠሪያ እንዲሆን ምን እንድርግ? እነዚህን ነው መተንተን፣ እነዚህን ነው መሥራት፣ እነዚህን ነው የሕዝብ ገንዘቦች ማድረግ፣ በእነዚህ ላይ ነው መግባባት ያለብን፡፡ ግድቡ መሠራት ያለበት በዜጎች ላይ ቀልደን ሳይሆን ዜጎችን በብቃት አሳምነን ነው፡፡  
 
ግድቡ ያልቃል፡፡ ወንዙም ይቀጥላል፡፡ የሚቀረው ታሪክና ሐሳቡ ነው፡፡ አሜሪካውያን በአሪዞናና በኔቫዳ መካከል የሚገኘውን የሁቨር ግድብን የሠሩት(እኤአ ከ1931-36) በችግር ወቅት ነው፡፡ ገንዘባቸው፣ ጉልበታቸውንና ዕውቀታቸው ሠውተው ነው የሠሩት፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ገንቢዎች ሕይወታቸው ከፍለውለታል፡፡ አያሌ አሜሪካውያን ዛሬ ግድቡን ለመጎብኘት ሲሄዱ ከግድቡ በላይ ስለ ግድቡ አሠራር የሚያሳየውን ሙዝየም መጎብኘት ነው የሚያስደስታቸው፡፡ ለምን ተገነባ? የዚያን ዘመን መሪዎችና ሕዝብ ምን ነበር ዓላማቸው? እንዴት ነበር የገነቡት? እነማን ምን ዓይነት መሥዋዕትነት ከፈሉ? ግድቡን ሲገደቡ አሜሪካን የት ማድረስ ነበር ሕልማቸው? ይህን ነው ሙዝየሙ የሚተርከው፡፡ የተሠው ዜጎችን፣ የቀን ራሽን እየተሰጣቸው የገነቡ አሜሪካውያንን፣ በአነስተኛ ክፍያ ለሀገራቸው የሠሩ ባለሞያዎችን ያሳያል ሙዝየሙ፡፡
 
ሁቨር ግድብ ለአሜሪካውያን ግድብ ብቻ አይደለም፡፡ የአልሸነፍ ባይነት መገለጫ፣ ሀገርን ከግል ጥቅምና ከጊዜያዊ ችግር በላይ አድርጎ ማሰቢያ፣ ብንወድቅ እንነሣለን፤ ‹ኢኮኖሚያችን ለጊዜው ቢወድቅም፣ እኛ ሕዝቦች ግን አልወደቅንም› የሚለውን የአሜሪካውያንን የዚያ ዘመን ፍልስፍና ማረጋገጫ ነው፡፡ ጽናታቸውንና የሀገር ፍቅራቸውን ማሳያ ነው፡፡ አስጎብኝዎቹ እንደሚሉትም ‹እንደ ሕዝብ አንወድቅም› የሚለውን ፍልስፍናቸው ማስመስከሪያ ነው፡፡ 
 
የሕዳሴው ግድብ ግን ‹የዚህ መሥሪያ ቤት ሠራተኞች ጎበኙት› ከሚለው ዜና በዘለለ ‹ስለምኑ› የማይወራለት፣ ፍልስፍናው የማይተነተንለት፣ ከግድቡ በላይ፣ ከአሸዋው፣ ከሲሚንቶውና ከብረቱ በላይ፤ ከጠጠሩና ከድንጋዩ ባሻገር ግድቡ ምንድን ነው? የሚለውን መግፍኤ ሐሳብ የሚናገርለት ያጣ ምስኪን ግድብ ነው፡፡ ልጆቻችን ነገ ግድቡን አይደለም የሚጎበኙት፡፡ እንዴት ተሠራ፣ ለምን ታሰበ፣ አባቶቻችን ምን ለውጥ ነበር ሊያመጡ ያሰቡት? የነበሩትን ተግዳሮቶች እንዴት አለፏቸው? የግድቡ መሠራትስ ምን የአስተሳሰብ፣ የአሠራር፣ የኢኮኖሚ፣ የባሕል፣ የዲፕሎማሲና የሀገር ገጽታ ለውጥ አመጣ? የሚለውን መመርመር ነው የሚፈልጉት፡፡ ከግድቡ ጀርባ የነበረውን የኢትዮጵያውያን ፍልስፍናና መንፈስ ነው የሚሹት፡፡  
 
ያ ሁሉ ቀረና፣ ጽድቁ ቀርቶ በወጉ እንኳን የሚኮንነው በማጣት …
 
ጭራሽ ሰሞኑን የምናያቸው ማስታወቂያዎች ደግሞ የግድቡን ሐሳብ አውርደው አውርደው ገንቦ ጠላና የብረት ምጣድ ጥብስ ላይ የሚጥሉ ሆኑ፡፡ ከዚህ በፊት ከጉንጭ የተረፈ ዳቦ በመብላት፣ በጎልማሶች ትምህርት ላይ በማሾፍ የተሠራውን ማስታወቂያ ስንታገሠው አሁን  ደግሞ  ‹ሕዳሴው ወርዶ ወርዶ› የጠላና የጥብስ መጨዋቻ ሆነ፡፡ ፀጉሯ እንኳን ወርዶ ወርዶ ‹ይጠቀለላል እንደ ሰርዶ› ነበር የተባለው፡፡ እንዴው ከዚህ የተሻለ ከፍ ያለ ሐሳብና የመንገሪያ መንገድ አጥተን ነው የግድቡን ሐሳብ በጋን ጠላና በብረት ምጣድ ጥብስ የምናሰቃየው? 
 
አሁን የሦስት ብር የስልክ ሎተሪን ለመግለጥ ‹መቼ ነው መብላት የሚጀመረው?›› ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል? መብላት ከተጀመረ ቆየ አይደለም እንዴ? መብላቱ አስቸግሮ አይደል እንዴ ፀረ ሙስና የሚባል መሥሪያ ቤት የተቋቋመው? አሁንኮ ሰው  መብላትንና መበላትን ለምዶት ‹ምናለ በልተው እንኳን ቢሠሩ› እያለነው፡፡›› የዐጸደ ሕጻናት አማርኛ ማስተማሪያ ይመስል ‹‹ጋን በጠጠር ይደገፋል›› የሚለውን አባባል ለማሳየት ጠላ የሞላ ጋን ማሳየት ያስፈልጋል? ግድቡ አሳዘነኝ፡፡ ‹እብድ የያዘው መልክ አይበረክትም› ማለት ይኼ ነው፡፡ 
 
ልጅቱ የሐር ነዶ የመሰለ ፀጉር ነው ነበራት አሉ፡፡ አልፈለገችውም፡፡ ፀጉር ቤት ገባችና ‹‹ቁረጭኝ›› አለቻት ፀጉር ሠሪዋን፡፡ ከከፈለቻት እርሷ ምን ተዳይዋ ልትመደምዳት ተነሣች፡፡ እዚያ ፀጉር ቤት ልትሠራ ገብታ የነበረች እናት ብትመክራትም ወጣቷ እምቢ አለች፡፡ ሴትዮዋም ‹‹ ይህን የመሰለ ፀጉር ማን እንዲህ ባለ ጭንቅላት ላይ ብቀል ብሎታል› አለች አሉ፡፡  
ሲሆን ‹በባሕል ትክክል ለመሆን› በዚህ ከፊሉ ሕዝብ በሚጾምበት ጊዜ የጥብስ ማስታወቂያ ባይኖር ጥሩ ነበር( የግድ መጠበስ ካለበት ወይም ጥብሱ በስፖንሰር የመጣ ካልሆነ)፡፡ ደግሞስ ከመቼ ወዲህ ነው ለገንቦ ጠላ የሚጋደሉ ጠጪዎች ሀገራዊ ለውጥ አምጥተው የሚያውቁት? ‹ዶሮ ብታልም ጥሬዋን› ሆኖ ካልሆነ በቀር፡፡ የሦስት ብር ሎተሪ ለማስቆረጥ በገንቦ ጠላ መጣላት አመልን በቴሌቭዥን መግለጥ ካልሆነ ምን ሊሆን ነው፡፡
 
ወይ ግድቡን ‹የሕዳሴ ግድብ› ብለን መጥራታችንን እናቁም፤ ወይ ማስታወቂያዎቻችን ግድቡን የሚመጥኑ ይሁኑ፡፡ ያን የመሰለ ታላቅ ሐሳብና የትውልድ ሥራ በገንቦ ጠላ፣ በብረት ምጣድ ጥብስ፣ በጉንጭ ሙሉ ዳቦ መቀለጃ አታድርጉት፡፡