አገራችን ኢትዮጵያ ያለችበትን አሳዛኝ ሁኔታ ከማንም የበለጠ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ይረዳዋል ብለን እናምናለን። የኢሕአዴግ መንግስት፣ ላያ ላዩን «በዴሞክራሲ አምናለሁ» ቢልም፣ ፍጹም አምባገነን በሆነ መልኩ ፣ ሕዝቡን አፍኖ፣ እያሰራ፣ እየገደለ፣ ዜጎችን እያፈናቀለ፣ ከሃያ አመታት በላይ ቆይቷል። በአብዛኛዉ ሕዝብ ዘንድ እየተጠላ፣ ይሄን ያህል አመት በስልጣን መቆየት የቻለው፣ አገዛዙ በዋናነት ኢትዮጵያዊያን መከፋፈል በመቻሉና ዜጎች ደፍረው ለመብታቸው እንዳይቆሙ በፍርሃት እንዲተበተቡ በማድረጉ ነው። ይሄንን ለማስቆም ሕዝቡን ማስተባበርና ማደራጀት ቀዳሚና ብቸኛ አማራጭ ነው።

አገር ቤት በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉ በርካታ የፖለቲካ ድርጅቶ አሉ። ከነዚህ ድርጅቶች መካከል አንዱ የአንድነት ፓርቲ ነው። የአንድነት ፓርቲ «የሚሊዮኖች ድምጽ ለፍትህ» እና «የሚሊዮኖች ድምጽ ለመሬት ባለቤትነት» በሚል ሰላማዊ እንቅስቃሴዎችን ለማድረግ ተዘጋጅቷል። ይህ እንቅስቃሴ የአንድ ፓርቲ እንቅሳቅሴ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ሕዝብ እንቅስቃሴ እንደመሆኑ፣ በአገራችን ዴሞክራሲና የስርዓት ለዉጥ እንዲመጣ የሚፈልጉ ዜጎች ሁሉ ሊቀላቀሉት፣ ሊደግፉት፣ የራሳቸው ሊያደርጉት የሚገባ እንቅስቃሴ ነዉ። ይህ እንቅስቃሴ የሚሊዮኖች እንቅስቃሴ ነው። የእያንዳንዳችን እንቅስቃሴ ነው።

በቅርቡ በባህር ዳር አስደናቂ ሰልፍ መደረጉ ይታወሳል። በቦታዉ የተገኙ ወገኖች ድምጻቸውን ያሰሙት አንድን ፓርቲ ብለው አልነበረም። ኢትዮጵያን ብለው ነዉ እንጂ። የባህር ዳሩ ሰልፉ ያማከለው በአንድ ድርጅት ዙሪያ አልነበረም። ነገር ግን በኢትዮጵያ ዙሪያ እንጂ። ይህ በባህር ዳር የተደረገውን አይነት የነጻነት እንቅስቃሴ በተጧጧፈ መልኩ በመላው አገሪቷ ማድረጉ አስፈላጊ ነው።

በአገሪቷ ሕገ መንግስት አንቀጽ 30 መሰረት፣ የዜጎች የመሰባሰብ ፣ በሰላም ትእይንተ ሕዝብ የማድረግ ሙሉ መብት የተረጋገጠ ነው። በመሆኑም ይህ የሚሊዮኖች ለነጻነት ንቅናቄ ሰላማዊና የአገሪቷ ሕግ በሚፈቅደው መሰረት የሚደረግ በማንም ዜጋ ወይንም ቡድን ላይ ያላነጣጠረ፣ የተወሰኑትን ጠቅሞ ሌላዉን የሚጎዳ ያልሆነ፣ በዘር፣ በሃይማኖት፣ በመደብ፣ በጾታ ልዩነት ሳያደርግ፣ ኢትዮጵያዉያንን በሙሉ ለፍትህና ለነጻነት ለማሰባሰብና ለማንቀሳቀስ ታሰቦ የታቀደ እንቅስቃሴ ነው።

በዳያስፖራ ያለው ማህበረሰብም የኢትዮጵያ ሕዝብ አካል እንደመሆኑ፣ የድርሻዉን መወጣት ይጠበቅበታል። በመሆኑም ይሄን የሚሊዮኖች ድምጽ ወይንም በባህር ዳር የተደረገዉን አይነት እንቅስቃሴ በሌሎች ከተሞች እንዲደረግ ለመርዳትና ለማጠናከር፣ የዳያስፖራ የሚሊዮኖች ድምጽ ግብረ ኃይል ተቋቁሟል። ይህ ግብረ ኃይል በዳያስፖራ ባሉ የአንድነት ፓርቲ ድጋፍ ማህበራት አነሳሽነትና በዉጭ ካሉ የአንድነት ፓርቲ ድጋፍ ማህበራት በተጨማሪ፣ ከተለያዩ የሲቪክ ማህበራት፣ አገር ቤት የሚደረገዉን ሰላማዊ ትግልን በሚደገፉ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ሲቪክ ማህበራት ፣ ፓልቶክ ክፍሎችና ግለሰቦች ተባባሪነት፣ «እኛም የሚሊዮኖች አንዱ አካል ነን» እያሉ ቀናና የሚያኮራ ኢትዮጵያዊ ምላሽ እየሰጡ ያሉና ለመስጠትም የተዘጋጁ፣ በአለም ዙሪያ ሁሉ ያሉ ኢትዮጵያዉያንን ለነጻነትና ለፍትህ ለማሰባሰብ የተዋቀረ ነው።

የሚሊየነሞች ንቅናቄ አዲስ አበባ እና ድረደዋ አስተዳደሮችን ጨምሮ፣ በኦሮሚያ የአዳማ፣ የላፍቶና የነቀምቴ ከተሞችን፣ በደቡብ ክልል፣ የአዋሳ፣ የጂንካና የቁጫ ወረዳዎችን፣ በትግራይ ክልል የመቀሌ ከተማን፣ በአማራዉ ክልል ደሴ፣ የወልዲያ፣ ደብረ ታቦር ፣ ደብረ ማርቆስ እና በምእራብ አርማጭሆ የአብርሃ ጅራ ከተማን ፣ በቤኔሻንጉል ጉሙዝ የአሶሳን ከተማ፣ በጋምቤላ ክልል የ ጋምቤላ ከተማ የሚያዳርስ ይሆናል።

የሚሊየምን እንቅስቃሴን በተመለከተ በየጊዜዉ ወቅታዊ መግለጫ የምንሰጥ መሆናችንን እየገለጽን። በዉጭ የሚገኘው ኢትዮጵያዊ እንደከዚህ በፊቱም ታላቅ ድጋፉን እንዲያበረክት በአክብሮት እንጠይቃለን። አገራችን ኢትዮጵያ የሁላችንም የጋራ አገር ናት። ለአገራችን መነሳታችን ሊያስከፋ የሚችለው፣ ወይንም ዝምታን ተስፋ ቆርጠን መቀመጣችን ሊያስደስት የሚችለው አምባገነኖችን ብቻ ነው። በሕዝባችን ላይ ግፍ የሚፈጽሙ አይደሰቱ። እንነሳ። የድርሻችንን እንወጣ። ከሚሊዮኖች አንዱ እንሁን !

በምትኖሩበት ከተማ ተደራጅታችሁ፣ ከዚህ ግብረ ኃይላ ጋር በመስራት በአገር ቤት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ስፖንሰር ማድረግ የምትፈልጉ በሚከተሉት አድራሹ ሊያገኙን ይችላሉ

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር !

[email protected]
404- 518-7858

“ዳውድ ኢብሳ ሲሞት ጥሩኝ” በሚል ርዕስ በለጠፍኩት አነስተኛ ሐተታ ላይ ሁለት ዓይነት ተቃውሞዎች ቀርበውብኛል፡፡ አንደኛው “ኦነግ በአማራው ላይ የሰራውን ሴራ እና ሸፍጥ እያወቅክ ጥብቅና ቆመህለታል” የሚለው ሲሆን ሁለተኛው “የኦፒዲኦን ድርጅታዊ ህልውና አንኳሰስክ፤ አቶ አለማየሁንም ረገጥክ” የሚል ነው፡፡ ስለ ኦፒዲኦ የጻፍኩት አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የድርጅቱ አባላት እራሳቸው በየአጋጣሚው የሚናገሩትን ነው በፌስቡክ የደገምኩት፡፡ በተለይ ደግሞ አባላቱ ከስራቸው ሲባረሩ፣ ወይ ደግሞ ከድርጅቱ ከድተው ወደ ውጪ ሀገር ሲኮበልሉ “ኦፒዲኦ የኦሮሞን ህዝብ ለማጭበርበር ሆን ተብሎ የተፈጠረ ድርጅት ነው” የሚል ጩኸት በማሰማት ነው የሚታወቁት፡፡ እነ ዮናታን ዲቢሳ፣ ዱባለ ጃሌ፣ ኢብራሂም መልካ ሲያደርጉት የነበረው ይህንኑ ነው፡፡ ነገር ግን እኔ የነርሱን ፈለግ በመከተል አይደለም እንዲያ ብዬ የጻፍኩት፡፡ ከነርሱ በፊትም እንደዚያ ስል ነበር፡፡
——
ኦነግን ለመጀመሪያ ጊዜ ካየሁበት ግንቦት 1983 ጀምሮ የድርጅቱን የፖለቲካ መስመር ስደግፍ ቆይቻለሁ፡፡ ዩኒቨርሲቲ ስገባ ግን ድርጅቱ በሚያራምደው ርዕዮተ ዓለምና በፖለቲካ ፕሮግራሙ ላይ ጥያቄዎች ማንሳት ጀመርኩ፡፡ በዋነኛነትም “የመገንጠል ፖለቲካው የኦሮሞን ጥያቄ የትም አያደርሰውም” የሚል ሀሳብ አነሳሁ፡፡ እንዲሁም የሚከተላቸው ስትራቴጂዎቹ ፍጹም ሊዋጡልኝ አልቻሉም፡፡ በዚህም ከኦሮሞ ወንድሞቼ ጋር ብዙ ጊዜ እነታረክ ነበር፡፡ በተለይም በዚያ ጊዜ ኦነግን መተቸት Taboo ተደርጎ ይቆጠር ስለነበር ከቅርብ ጓደኞቼ ጭምር እስከመጣላት ደርሰናል፡፡ እናም ከ1990 ጀምሮ የድርጅቱ ተቃራኒ እንጂ ደጋፊ አይደለሁም፡፡

እንዲህ በመሆኑ ግን ድርጅቱን በሐሰት መክሰስ ያለብኝ አይመስለኝም፡፡ ድርጅቱን በሰራው ጥፋት ብወቅሰው ማለፊያ ነው፡፡ ባልሰራው ወንጀል መክሰስ ግን ለማንም የሚበጅ አይሆንም፡፡ እንደምሳሌም ኦነግ የሚከሰስባቸውን ጭፍጨፋዎች እንመልከት፡፡ በደኖ፣ አርባ ጉጉ፣ ወተር፣ አረካ፣ አሰቦት ገዳም ወዘተ…

እነዚህ ጭፍጨፋዎች መከሰታቸው ሁላችንንም ያሳዝነናል፡፡ አንድ ቀን እውነቱን ፈልፍለን የማውጣት ግዴታም ተጥሎብናል፡፡፡ ነገር ግን በርካታ ሰዎች በሁሉም ጭፍጨፋዎች ኦነግን ተጠያቂ ሲያደርጉ በጣም እገረማለሁ፡፡ በተለይም ዛሬ በህትመት ላይ የሌሉ ሁለት የግል ጋዜጦች ይህንን ፕሮፓጋንዳ እየደጋገሙ ሲያስተጋቡት ሳይ “ስለ የትኛው ሀገር ነው የሚያወሩት” እያልኩ እደነቅባቸው ነበር፡፡ እንዲህ የምለው ጋዜጦቹ የመረጃ እጥረት የነበራቸው መሆኑን በማወቄ ብቻ አይደለም፤ የጂኦግራፊ እውቀትም ያጠራቸው ስለሚመስለኝም ጭምር ነው፡፡ ለምሳሌ “አረካ”ን እንውሰድ፡፡ ይህቺ ከተማ የት ነው ያለችው? ኦሮሚያ ውስጥ ነው? ወይስ ሌላ ቦታ?

ይገርማል! አረካ ማለት በደቡብ ክልል በወላይታ አውራጃ ከሶዶ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ ያለች ከተማ ናት፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ኦነግ እዚያ ድረስ ሄዶ ሀገር አላስተዳደረም፡፡ “አረካ የኦሮሚያ ግዛት ናት” ብሎ የሚያውቅም አይመስለኝም፡፡ እናም ጂኦግራፊን በትክክል የሚያውቅ ጋዜጠኛ የአረካውን ግጭትና ጭፍጨፋ ለኦነግ አይሰጥም ነበር፡፡ በተጨማሪም የአረካው ግጭት የደረሰው ኦነግ የሽግግር መንግሥቱን ለቆ ከወጣና በእጁ የነበሩት መሬቶች በሙሉ በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር ከወደቁ በኋላ ነው፡፡

የአረካው ግጭት በሽግግሩ ዘመን ለነበረው የተወካዮች ምክር ቤት የውይይት አጀንዳ ሆኖ እንደቀረበ ይታወሳል፡፡ በከተማዋ ያለቁት የ31 ሰዎች ግድያ በመከላከያ ሰራዊቱ እንደተፈጸመ መንግሥቱ በይፋ አምኗል፡፡ ዳሩ ግን ለግድያው የተሰጠው ምክንያት በጣም አነጋጋሪ ነበር፡፡ መንግሥት ያቀረበው ምክንያት “ሰልፈኞቹ የተገደሉት ቦንብ በመወርወራቸው ሳቢያ የመከላከያ ሰራዊቱ ራሱን ለመከላከል በወሰደው እርምጃ ነው” የሚል ነው፡፡ ይሁንና ይህንን ምክንያት ብዙዎች አልተቀበሉትም፡፡ ብዙዎች እንደተጠራጠሩት እስከ ዛሬ ድረስ ቆይቷል፡፡ በነገራችን ላይ በአረካ የሞቱት የቀድሞ መንግሥት ወታደሮች ነበሩ፡፡ እነዚያ ወታደሮች “የጡረታ መብታችን ይከበርልን” በማለት የተቃውሞ ሰልፍ በማድረጋቸው ነው ከመከላከያ ሰራዊቱ ጋር የተጋጩት፡፡
——–
በሚያዚያ ወር 1984 በወተር ከተማ በተካሄደ ጭፍጨፋ የሞቱትም በተመሳሳይ መልኩ በመከላከያ ሰራዊቱ እንደተገደሉ የሽግግር መንግሥቱ በወቅቱ አምኗል፡፡ ይሁን እንጂ በወተር የተገደሉት 230 ሰዎች በሙሉ ኦሮሞዎች እንጂ አማራዎች አልነበሩም፡፡ እነዚያ ሰዎች የተገደሉት ኢህአዴግ ከከተማቸው ወጥቶ ኦነግ ወደ ከተማዋ እንዲመለስ በመጠየቃቸው ነው (ወተር ለአንድ ዓመት ያህል በኦነግ ቁጥጥር ስር ነበረች፤ ኦነግ ከከተማዋ ሲወጣ ኢህአዴግ ገብቶባታል፤ ነዋሪዎቹ “እንደ ቀድሞው ጊዜያችን ኦነግ ወደ ከተማዋ ይመለስ” በማለታቸው ነው ከመከላከያ ሰራዊቱ ጋር የተጋጩት)፡፡ ጋዜጦቹ ግን “ኦነግ አማራዎችን ጨፈጨፈ” እያሉ ነበር የሚዘግቡት፡፡
——-
በ1984 (ወሩን አላስታውሰውም) በአሰቦት ገዳም በተካሄደ ግድያ ሰባት መነኮሳት ሞተዋል፡፡ ይህንን ግድያ የፈጸሙትም በወቅቱ የአሰቦት ከተማን ለትንሽ ጊዜ ተቆጣጥሮ የነበረው የኦሮሞ ነጻነት እስላማዊ ግንባር (IFLO) ታጣቂዎች ነበሩ፡፡ ግድያው ስር ሳይሰድ በአፋጣኝ ያስቆሙት ደግሞ ኢህአዴግና ኦነግ ነበሩ፡፡ ሁለቱ ድርጅቶች አንድ ጥምር ኮሚቴ በማቋቋም በወሰኑት ውሳኔ መሰረት IFLO ከከተማው ተባርሮ አካባቢው በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር እንዲውል ተደርጓል፡፡
——
በአርባ ጉጉ የተፈጸመው እልቂት በሁለት ተጎራባች መንደሮች መካከል በተካሄደ ግጭት ነበር የተለኮሰው፡፡ እያደር ግን መርቲ ጀጁ እና አሰኮ የሚባሉ የአርባ ጉጉ ወረዳዎችን አዳርሷል፡፡ በግጭቱ የኦሮሞ እና የአማራ ተወላጆች በእኩል ደረጃ ተጎድተዋል፡፡

በአርባ ጉጉ ግጭት የራሳቸውን የፖለቲካ ትርፍ ለማጋበስ የፈለጉ ወገኖች እጃቸውን አስገብተውበታል ይባላል፡፡ በመሆኑም በውጤቱ ከሁሉም ግጭቶች የከፋ ሊሆን ችሏል፡፡ በዚህ ግጭት ከሁለቱም ወገን እስከ ስድስት መቶ ያህል ሰዎች መሞታቸው ይነገራል፡፡ ከመቶ ሺህ ያላነሰ ሰው ወደ ሀረርጌና ሸዋ ክፍለ ሀገሮች ተፈናቅሏል፡፡ ሆኖም ኦነግ በዚህ ግጭት ውስጥ እጁን ማስገባቱን የሚያረጋግጥ ፍንጭ እስከ አሁን ድረስ የለም፡፡ ኦነግ በወቅቱ በአርባ ጉጉ አውራጃ ምንም ይዞታ አልነበረውም፡፡ የመላው አማራ ህዝብ ድርጅትም ቢሆን በግጭቱ የከሰሰው ኦህዴድን (OPDO) እንጂ ኦነግን አልነበረም፡፡ በተለይም እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የምዕራብ ሸዋ ፖሊስ መምሪያ ሃላፊ የነበረው ኮሎኔል ዲማ ጉርሜሳ ከግጭቱ ጋር ተያይዞ ስሙ በሰፊው ይነሳ እንደነበረ ይታወሳል፡፡ በዚያን ጊዜ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ሐሰን ዓሊ ከእፎይታ መጽሔት ጋር (ግንቦት 1985) ባደረጉት ቃለ-ምልልስ “አቶ ዲማ ጉርሜሳ ንጹሕ ነው” በማለት ከመከላከላቸውም በላይ ለግጭቱ ዋነኛ ተጠያቂ ያደረጉት መአሕድን እንጂ ኦነግን አልነበረም፡፡

የግል ጋዜጦች ግን ነገሩን አራግበው በኦነግ ላይ አላከኩት፡፡ ነገሩን ሳያውቁት ቀርተው የተደረገ አይመስለኝም፡፡ አንዳንድ ጋዜጦች -ተከፍሎአቸው እንዲህ እንደሚያደርጉ በደንብ እናውቃለን፡፡
——–
የበደኖ ጭፍጨፋ! አዎን! ኦነግ ሊጠየቅበት የሚገባው ብቸኛው ትራጄዲ ይህኛው ነው፡፡ በርግጥም እልቂቱ በተፈጸመበት ወቅት በደኖ በኦነግ ቁጥጥር ስር ነበረች፡፡ የሞቱት ሀምሳ ያህል ሰዎች ለምን እንደተገደሉ ባይታወቅም አድራጎቱ በኦነግ ወታደሮች እንደተፈጸመ ድርጅቱ ራሱ አምኗል፡፡ ኦነግ በወቅቱ በወታደሮቹና በአዛዦቹ ላይ እርምጃ ወስጃለሁ ቢልም የተወሰደውን እርምጃ ምንነት አልገለጸም፡፡ በነገራችን ላይ በዚህኛውም እልቂት ከሞቱት መካከል ግማሽ ያህሉ ኦሮሞዎች ነበሩ፡፡
—–
ከላይ በዝርዝር እንዳስረዳሁት የኦነግ ጭፍጨፋ ተብለው ከሚጠቀሱ ትራጄዲዎች መካከል አብዛኛዎቹ በኦነግ የተፈጸሙ አልነበሩም፡፡ ኦነግ ሊጠየቅበት የሚገባው ብቸኛው ድርጊት በበደኖ የተፈጸመው ነው፡፡ የእውነት ቀን ሲመጣ ያንን ፋይል ማውጣታችንም አይቀሬ ነው፡፡ ይሁንና በኦነግ ያልተፈጸመውን ከርሱ ጋር አያይዞ መጻፍ ጥቅሙ ምን እንደሆነ ሊገባኝ አይችልም፡፡ እንዲያውም የያኔዎቹ የግል ጋዜጦች የሚያራግቡት ወሬ በተወሰነ መልኩ የኦነግ ጨካኝነትን ከመግለጽ ይልቅ “ኦሮሞ ጨካኝ ነው” የሚል እድምታ ለመፍጠር የታለመ ነበር የሚመስለው፡፡

እርግጥ የኦነግ ወታደሮች በብዙ አጋጣሚዎች ልዩ ልዩ የጭካኔ ተግባራትን ሲፈጽሙ ተስተውለዋል፡፡ እርሱን አንክድም፡፡ የነርሱ ገፈት ቀማሽ ሆኖ የዘለቀው ግን በአብዛኛው ኦሮሞው ነው እንጂ የሌላ ብሄረሰብ ተወላጅ አልነበረም፡፡ በተለይ አንዳንዶቹ የኦነግ ወታደሮች “ጎበና፤ ቢተምቱ.፤ ወዘተ..” ለሚሏቸው ግለሰቦች ምህረት አልነበራቸውም፡፡ እንዲሁም ተጻራሪ ድርጅት ሊያቋቁሙ ነው በሚል ፍርሃት አባላቶቻቸውን ጭምር እስከ መግደል ይደርሱ ነበር (የኦነግ የሀረር ቢሮ ሃላፊ የነበሩትን አቶ አራርሶ ወዳይን እና በመቻራ ከተማ የተገደለውን የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ምሩቅ ካሊድ ሃጂ ኑራን መጥቀሱ ይበቃል)፡፡ ሆኖም ጋዜጦቻችን ድርጅቱ የፈጸመውን ማውራት ይተውና ድርጅቱ ያልፈጸመውን ወንጀል ይነግሩን ነበር! ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ማለት ይህ ነው፡፡

ለማጠቃለል ያህል እኔ ለኦነግ አልተከላከልኩለትም፡፡ አንዳች ጥብቅና አልቆምኩለትም፡፡ የጻፍኩት የማውቀውን ሐቅና የማምንበትን አቋሜን ነው፡፡ ይሁንና ይህ አባባሌ ኦነግን ከመፍራት እንዳይወሰድብኝ አደራ እላለሁ! አስፈላጊ ከሆነ በኦነግም የተፈጸሙ ስህተቶችና ጥፋቶችን አንድ በአንድ መዘርዘር እችላለሁ፡፡

ሰናይ ቀን ይሁንላችሁ!!

[ውንብድና ካርቱም በሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ]

ሁዳ የሚባል እስር ቤት 35 ጠያቂ የሌላቸው እስረኞች ይማቅቃሉ – አብርሃ ደስታ ከመቀሌ

በዓለም ዉድድር አለ። ዉድድሩ በህዝቦች መካከል ነው። ህዝቦች ዉድድሩን ለማሸነፍ አብሮነትን ይፈልጋሉ። በአብሮነት የራሳቸው ደህንነትና ጥቅም ማስከበር ይሻሉ። ደህንነታቸውንና ጥቅማቸው ለማስከበር ሀገር ይመሰርታሉ። ሀገር መስርተው በመንግስት ይወከላሉ። የመንግስት ተግባር ታድያ የህዝቡን ጥቅምና ደህንነት መጠበቅ ነው። በዚሁ መሰረት መንግስት የህዝቦች ተወካይ ጠበቃ መሆን ይጠበቅበታል።

የህዝቦች ወኪል (ጠበቃ) ለመሆን መንግስት በተለያዩ ሀገሮች ኤምባሲ ይከፍታል። የኤምባሲው ሰራተኞች የሚወክሉትን ህዝብ ጥቅምና ደህንነት ይጠብቃሉ፣ ያስጠብቃሉ። ለዚሁ ተግባራቸው ሲባል ህዝብ ደሞዛቸውን ይከፍላቸዋል። ደሞዛቸው የሚከፈላቸው ከመንግስት ካዝና ነው። የመንግስት ገንዘብ የሚሰበሰበው ከህዝብ ነው፤ በግብር መልክ።

ካርቱም የሚገኙ ጓደኞቼ እንደላኩልኝ ከሆነ የኢትዮጵያ ኤምባሲ (በካርቱም) ሰራተኞች በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ተግባር ተሰማርተው ኢትዮጵያውያንን አደጋ ዉስጥ እየጣሉ ይገኛሉ። የሰዎች ደህንነት ከመጠበቅ ይልቅ ሰዎችን አደጋ ዉስጥ ማስገባት ምን ይሉታል? የመንግስት አካላት ወንጀልን ከመከላከል ይልቅ ቁማርተኞች ሲሆኑ ምን ማድረግ ይቻላል?!
የኢትዮጵያ መንግስትም (መንግስት ልበለው) ከህዝብ ኪስ የሚከፈሉ የኤምባሲ ሰራተኞች አሉት። በተለያዩ ሀገሮች ያሉ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች በህዝብ ገንዘብ እየተዳደሩ የሚከፍላቸውን ህዝብ የሚበድሉ መሆናቸው እናውቃለን። ዛሬ ትኩረቴ የሳበ ግን በካርቱም ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ነው።

የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች ሱዳን ዉስጥ የሚቸገሩ ዜጎቻችንን ደህንነት ከመከታተል ይልቅ ከሱዳን መንግስት ጋር በመተባበር ኢትዮጵያውያን እስርቤት ይከታሉ። እስካሁን ድረስ በሱዳን ብዙ ኢትዮጵያውያን ያለ ምንም ጠያቂ በወህኒቤቶች እየማቀቁ ነው። የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች በሱዳን ሀገር የሚደርስባቸው ችግር፣ እስር፣ እንግልት እያወቁ በሰዎች ንግድ መሰማራታቸው ይገርማል። የኤምባሲው ሰራተኞች በሀገራቸው ሰዎች ንግድ ነው የተሰማሩ።

በሱዳን ያሉ ኢትዮጵያውያን መንግስት እንደሌላቸው (መንግስት አልባ እንደሆኑ) ነው የሚቆጠረው። “ሑዳ” በሚባል ወህኒቤት 35 ጠያቂ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን አሉ። እነዚህ እስረኞች ያለ ምንም የፍርድቤት ዉሳኔ የተያዙና ከ8-12 ዓመት በወህኒቤቱ የቆዩ ናቸው። ተሰቅለው የተገደሉም መዓት ናቸው። በሱዳን የኢትዮጵያውያን ህይወት ርካሽ ነው። መስከረም አያሌው የተባለችም በሰባት ሱዳናውያን መደፈሯ ይታወሳል።
ኢትዮጵያውያን መንግስት አልባ (stateless) ሁነው ሲሰቃዩ የኤምባሲው ሰራተኞች ግን ሰዎች እየገዙና እየሸጡ (በሰዎች ንግድ ተሰማርተው) ገንዘብ ይሰበስባሉ። ዘመናዊ መንግስታዊ የንግድ ባርያ መሆኑ ነው።

ኢትዮጵያውያን ክብራችንን የምናስመልስበት ግዜ ሩቅ አይሆንም። አቶ መሐመድ ቱፋና አቶ በላቸው ግን ተግባራቹሁ ሁሉ እየተከታተልነው እንገኛለን።

ምንሊክ ሳልሳዊ ፦ህዝብ በኢኮኖሚ ሲጐሳቆል፣ በፖለቲካ በደል ሲሰማውና በማህበራዊ ህይወቱ ያልተረጋጋ ከሆነ ደግ አደለም፡፡ በጥንቱ ማርክሳዊ አካሄድ ፖለቲካ ማለት የተጠራቀመው የኢኮኖሚ ይዘት ነፀብራቅ/መገለጫ እንደማለት ነው፡፡ በግድ አራምደዋለሁ ካሉ አንገት መቀጨት፣ መሰበር፣ መውደቅ፣ አልጋ ላይ መቅረት ይከተላል ማለት ነው፡፡ ለማደግ አቅጣጫ ያስፈልጋል፡፡ ከመዓቱ ለማምለጥ መፍጠንም ያስፈልጋል፡፡ አቅጣጫ ማወቅ ብቻ ሳይሆን መሮጥና መፍጠን ያስፈልጋል ስንል ግን፣ ከምን አቅም? በምን ነፃነት? በምን ፍትሐዊ እርምጃ? በምን ዓይነት ቢሮክራሲያዊ ተቋም? በምን ዓይነት እርስበርስ መተማመን? በምን ዓይነት የገዢ ተገዢ ግንኙነት? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡

የአስተዳደር ነገር መቼም ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ኢኮኖሚያችን በኑሮ ውድነቱ መነጽር ሲታይ ዛሬ አሳሳቢ ነው፡፡ የሁሉም ነገር ዘዴው ተገኝቷል እንዴት እንደምንኖር መላው ከመጥፋቱ በስተቀር ፡፡ለፍቶ ለፍቶ፣ ዳክሮ ዳክሮ ኑሮ ጠብ አልል ያለው ሰው ከምሬት ሊወጣ አይችልም፡፡“እምዬ ኢትዮጵያ ሥራሽ ብዙ ፍራንክሽ ትንሽ” አለ አሉ አንድ ሠራተኛ! በእርግጥ በሊቀ – ሊቃውንት አስተሳሰብና ስሌት “ከአምስት አመት በኋላ ሠንጠረዡ ከፍ ይላል”፤ “በ2017 ዓ.ም አያሌ ፕሮጄክቶች ስለሚጠናቀቁ የተለየ ዓለም ይታያል” ወዘተ ይባላል፡፡ ምንሊክ ሳልሳዊ ችግሩ ህዝባችን “ሰብል በጥር ይታፈሳል” ቢሉት “ሆዴን እስከዚያ ለማን ላበድረው” አለ፤ የሚባለው ዓይነት ችግር ውስጥ ይገባል፡፡ አጣብቂኙ ከባድ ነው፡፡ ያለፈው ዘመን መሪ “የወረቀቱ ገብቶኛል፡፡ የገበያውን፣ የመሬት ያለውን ጉዳይ አስረዱኝ” አሉ አሉ፡፡ በግራፍ (ሠንጠረዡ ላይ) ሰብሉ ሰማይ ነክቶ፣ ከገበያው ግን ጠፍቶ ሲያዩት ቢጨንቃቸው ነው፡፡

የአመራራችንን ጉዳይ ችላ ብለን፣ የቢሮክራሲውን አካሄድ ወደጐን ትተን፣ ወደየትም የተሻለ ህይወት መዝለቅ አንችልም፡፡ በአካላችን እያወደስን በሆዳችን እየሰደብን የቱንም ወንዝ አንሻገርም፡፡ የምርጫችንን የዲሞክራሲያችንን ነገርም አደራ መባባል ያለብን ጊዜ ነው፡፡ መጽሐፍ ከመፃፍ፣ አዋጅ ከማወጅ፣ መመሪያ ከማውጣትና ጋዜጣዊ ጉባዔ ከማካሄድ አልፈን በቀናነት ለህዝባችን የሚበጀው ማንኛው መንገድ ነው? ማለት በጐ ነገር ነው፡፡

በኢኮኖሚያዊ ገቢያችን፣ በፖለቲካዊ መልካም አስተዳደራችን፣ በማህበራዊና ባህላዊ ማንነታችን የሚደርስብንን ጉስቁልና አሸንፈንና ድህነታችንን ታግለን በሁሉም አቅጣጫ ለውጥ እናመጣ ዘንድ፤ የህዝብ መነሳሳትን የሚያህል ካፒታል የለም፤ መነሳሳት ተገቢ ነው! አለበለዚያ ትላንት የነበርንበት ቦታ እንደተመቸን ቆጥረን መቀበል “ያደሩበት ጭቃ ከጭድ ይሞቃል” የሚለውን ተረት ከማረጋገጥ በቀር ፋይዳው በድን ነው፡፡

በትዕዛዝ እንግዳ ከመቀበል ይሰውረን፡፡ ባህላዊ እንግዳ – ተቀባይነታችንን ይባርክልን፡፡ ከጐረቤት ጋር ከመጣላት ይሰውረን፡፡ ተጣልተን ከታረቅንም ዕውነቱን የሚነግረን አያሳጣን፡፡ ስንጣላ መፈክር ከማስነገርና ከመራገም፤ ስንታረቅ ከማጨብጨብ ይሰውረን፡፡ የመንግስታችንን ልብና ልቦና እናውቅ ዘንድ የመረጃ ደሀ አያድርገን! የምንሰማውን በሌላ እንዳንተረጉም ንቃተ – ህሊናውን ያድለን ዘንድ፤ የሰላምና የማስተዋል ያድርግልን፡፡ ብሶት ሁሉ የፈጠራ፣ ጩኸት ሁሉ የሁከት፣ ሥጋት ሁሉ የትርምስ፤ እንዳያስመስልብን አስተዋይ ተመልካች ይሰጠን፡፡ ማየት – የተሳነው ተመሪ እንዳይሸበር ነገሩን ግልጥልጥ የሚያደርግ መሪ ይባርክልን፡፡ምንሊክ ሳልሳዊ

በጅጅጋ 300 እስረኞች መንገድ ላይ ተጣሉ

በጅጅጋ እስር ቤት ውስጥ ታስረው ከነበሩ ቁጥራቸው በውል ከማይታወቅ እስረኞች መካከል 300 ያክሉ ከአራት ቀናት በፊት በጅጅጋ መንገድ ላይ መጣላቸው ታውቀ።

የኦጋዴን ነጻ አውጭ ድርጅት ያላከውን መረጃ በመንተራስ ኢሳት ባደረገው ማጣራት፣ ባለፈው ሃሙስ ለአርብ አጥቢያ አካላቸው በምግብ እጦት የከሳ፣ አይናቸው የታወረ፣ እግሮቻቸው ሽባ የሆኑ፣ የአእምሮ መታወክ የደረሰባቸውና አሰቃቂ የእስር ቤት ህይወት እንዳሳለፉ የሚናገሩ እስረኞች በጅጅጋ ጎዳናዎች ላይ ተጥለዋል።
ከተጣሉት መካከል ወላጅ አልባ የሆኑ ምናልባትም በእስር ቤት ውስጥ የተወለዱ ህጻናት፣ ወጣቶችና አዋቂዎች ይገኙበታል።

አብዛኞቹ እስረኞች ከሰውነት ተራ የወጡና በበሽታ የተጠቁ እንዲሁም ለረጅም ጊዜ በእስር ቤት ውስጥ የቆዩ ናቸው። ኢሳት ለማረጋገጥ ባይችልም፣ የኦብነግ መረጃ እንደሚያሳየው ከተፈቱት እስረኞች መካከል 20ዎቹ በሶስት ቀናት ውስጥ በበሽታ ሞተዋል።
ከአንድ ወር በፊት ኢሳት ከጅጅጋ ከተማ 25 ኪሜትር ርቆ በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ በኮሌራ በሽታ ከ40 በላይ ሰዎች ሞተው በእስር ቤቱ አካባቢ አግባብ ባልሆነ መንገድ በመቀበራቸው አስከሬናቸውን ጅቦች እያወጡ በመብላታቸውና እና አካባቢው በበሽታ በመበከሉ በድጋሜ እንዲቀበሩ መደረጉን ዘግቧል።

የክልሉ መንግስት አሁን የወሰደው እርምጃ በእስር ቤቶች ውስጥ የተነሳውን የኮሌራ በሽታ ለመከላከል እንደሆነ እየተነገረ ነው።
በሶማሊ ክልል የተካሄደውን የብሄር ብሄረሰቦችን ቀን አስመልክቶ የክልሉን ገጽታ ያበላሻሉ የተባሉ ከ700 በላይ የጎዳና ላይ ተዳዳሪዎችና መታወቂያ የሌላቸው ሰዎች እንዲታሰሩ መደረጉ ይታወቃል።በጉዳዩ ዙሪያ የክልሉን የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊ ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም። ማጋቢት ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና

Image
እንደልቡ/ዳግም (ከቫንኮቨር፣ ካናዳ)

አባ መላ ማን ነው?

በቅጽል ስሙ “አባ መላ” በእውነተኛ ስሙ ደግሞ ብርሃኑ ዳምጤ ተብሎ ይጠራል፣ በ60ዎቹ የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ አዛውንት ነው (ምንም እንኳ ስራው እንደ እድሜው ባይሆንም)። ፓልቶክ የሚባለውን የማህበራዊ መገናኛ መድረክ በመጠቀም በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ዲስኩር በማሰማት ይታወቃል። በወጣትነቱ ኢህአፓ ውስጥ ነበር የሚባለው ብርሃኑ ዳምጤ ወዲያውም የኢህአፓን መዳከም አይቶ ወደ ደርግ ቡድን መቀላቀሉን የሚያውቁት ይናገራሉ። በወቅቱ አብረውት በኢህአፓ ውስጥ ይሳተፉ የነበሩ ወጣቶችን ለደርግ በእጅ መንሻ መልክ አሳልፎ ሳይሰጥ እንዳልቀረ በደርግ ካድሬነት ቆይታው የሚያውቁት ይጠረጥራሉ አንዳንዶች ደግሞ አፋቸውን ሞልተው ይናገሩታል።

ብርሃኑ ዳምጤ ከደርግ መውደቅ በኋላ በስደቱ ዓለም (ዳያስፖራ) ፖለቲካ መድረክ ብቅ ያለው በምርጫ 97 ወቅት የዝነኛውን ቅንጅት ማልያ ለብሶ ነበር። ይሁንና በስልጣን ላይ ያለው የህወሃት/ወያኔ መንግስት ምርጫውን አጭበርብሮ፣ የምርጫውን መጭበርበር የተቃወሙትን በገፍ በአደባባይ በጥይት ደብድቦ፣ ህዝቡ የመረጣቸውን የቅንጅት አመራሮች፣ ጋዜጠኞችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን ጨመሮ ከ50 ሺህ በላይ ባብዛኛው ወጣቶችን አስሮና በየጦር ካምፖቹ አጉሮ በአምባገነንነቱ ለመቀጠል ሲወስን ብርሃኑ ዳምጤም ባፋጣኝ የቅንጅትን ማልያ አውልቆ የህወሃት/ኢህአዴግን ማልያ ለብሶ ቁጭ አለ።

ሰሞኑን ደግሞ ብርሃኑ ዳምጤ አስደናቂ መገለባበጥን ፈጽሞ የህዝብን አይን አስበልጥጧል። እነዚህ ብርሃኑ ዳምጤ (አባ መላ) ሰሞኑን የሚፈጽማቸው መገለባበጦች በ1960ዎቹ እና 70ዎቹ ከነበሩት የመገለባበጥ ትሪኢቶቹ ለየት የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር አሁን መገለባበጡን የሚፈጽመው በቀጥታ ስርጭት ወቅት (በፓልቶክ) መሆኑና ጉዳዮን በመሪ ዜና መልክ የሚዘግብለት የቴሌቪዥን ጣብያ “ኢሳትን” ማግኘቱ ነው።

ብርሃኑ ዳምጤ ከጥቂት ወራቶች በፊት ነበር የተሰለፈበት የህወሃት/ኢህአዴግ ጎራ በተለይም ከወያኔው ቁንጮ መለስ ዜናዊ ሞት በኋላ እየተዳከመ መምጣትን አይቶና ገምቶ ወያኔዎችን “አፍንጫችሁን ላሱ፣ እኔ ከአሁን ብኋላ የድሮው አባ መላ አይደለሁም፣ እንዲያውም ጉዳችሁን አዝረጠርጣለሁ…” በማለት ፉከራ ቢጤ አሰምቶ የዲሞክራሲና የነጻነት ታጋዮችን ጎራ መቀላቀሉን ያበሰረው።

መንፈቅ እንኳ ሳይሞላ አባ መላ በመጣበት አይነት መንገድ ተመልሶ ህወሃት/ኢህአዴግን ለማገልገል መወሰኑን ይፋ አደርጓል። ለሱ እምብዛም አዲስ ያልሆነውን የክህደት ቁልቁለትም ዳግም ተያይዞታል።

አባ መላ፣ ኢሳትና ዳያስፖራው

የኢሳት ጋዜጠኞች፣ አንዳንድ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና የተቃዋሚ ፖለቲከኞችም ጭምር ይህ አባ መላ የሚባለውን ቦታ እየቀያየረ ይሚጫወት ዝቅተኛ ካድሬ ከሚገባው በላይ ቦታ ሰጥተውት እንደነበር እገምታለሁ፣ በውጤቱም ተከታዮቻቸውን ያሳሳቱና ያዘናጉ ይመስለኛል። ይህንን ጉዳይ ማንሳቴ “ብዬ ነበር” ለማለት ሳይሆን ይልቁኑም ይህ ክስተት እንደ መማሪያ ሆኖ እንዲያልፍ በመፈልጌ መሆኑን አባብያን እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ።

እንደ አባ መላ አይነቱ ቀደም ሲል በተደጋጋሚ የመገለባበጥ ብቃቱን ያሳየ ወለፈንዴ ተቃዋሚ ጎራ ገብቻለሁ ሲል አያያዛችን ጥንቃቄ የተሞላበት፣ ሊሆን ይገባል። በቅርቡ ተገልብጦ ሊያሳፍረን ይችላል ብሎ መስጋት፣ ለጉዳዩ መጠነኛ የአየር ሰዓት መስጠትና ውሎ አድሮ ደግሞ መርጋቱን እያዩ ወደሌላው መተላለፍ ተገቢ ነው። እንደው በአንድ ጊዜ ይህን ከምላስ በስተቀር ቁም ነገር የሌለው ተራ ካድሬ ወደላይ ቆልሎ አንድ ጊዜ “አክቲቪስት” ሌላ ጊዜ ደግሞ “የፖለቲካ ተንታኝ” እያሉ በኢትዮጵያውያን ስም በዓለም አቀፍ ደረጃ የተቋቋመ ግብረ ሰናይ ድርጅትን እንዲመራ ማጨት ድረስ መጓዙና አሉ ከሚባሉ ፖለቲከኞች ጋር መድረክ እንዲጋራ ሁኔታዎችን ማመቻቸቱ አገባብ አልነበረም።

የኢሳት ባልደረባ ደረጀ ሃብተወልድ የአባ መላን መገልበጥ አስመልክቶ በፌስቡክ ገጹ ላይ እንዳሰፈረው ከሆነ ግን ኢሳቶች ከስህተቶቻቸው ሊማሩ የተሰናዱ አይመስልም ይልቁኑም አባ መላን አስመልክቶ ሊቀርቡ የሚችሉ ትችቶችን ቀድሞ ለመከላከል ነው ሙከራ የሚያደርጉ ያሉት። ደረጀ ሃብተወልድ እንዲህ ነበር ያለው፣

“ነገሩ ወዲህ ነው። አባ መላ ኢህአዴጎችን እየሰደበ ወደ ተቃዋሚው ጎራ ሲቀላቀል “አገኛለሁ” ብሎ ያሰላው ጥቅም ነበር። ሆኖም ሀሳብን በነፃነት ለመግለጽ ከሚያስችል ነፃ መድረክ ውጪ ሌላ ነገር ሊያገኝ አልቻለም። ባገኘው ነፃ መድረክም ማንም ሳይቆነጥጠው ከትንሽ እስከ ትልቅ የቀድሞ አለቆቹን እስከ ዶቃ ማሰሪያቸው ነግሯቸዋል። እኛንም አስቆናል። ስንስቅለት ጨምሮ ጨማምሮ አቅምሷቸዋል። እኛም፦“የአገሩን ሰርዶ ባገሩ በሬ” እያልን ተዝናንተናል። ከዚያ ባለፈ ግን ለቁም ነገር ያሰበው ሰው ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ።”

የደረጀን አባባል ሁሉም ሰው የተቀበለው አይመስልም ይህን ለማሳየት ከተቃውሞ ሃሳቦች መካከል አንዱን ከዚያው ከደረጀ ሃብተወልድ የፌስቡክ ገጽ ልበደር፣

“የአባ መላን መገልበጥ ተከትሎ ኢሳቶች ከተወቃሽነት ለመዳን የዘየዳችሁት ይሄው ነው? ደረጀ “አባ መላን ለቁም ነገር ያሰበው ያለ አይመስለኝም” ያልከው ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው፣ በሳውዲ ወገኖቻችንን ለመታደግ በተቋቋመው አለም አቀፍ ድርጅት ውስጥ ከታማኝ እና አበበ ገላው ቀጥሎ ሶስተኛ ሰው ተደርጎ አልነበረም? በጣም ብዙ ማለት ይቻላል… “እጄን በጄ” ሆኖብን እንጂ። ለማንኛውም ከስህተቶቻችሁ ተማሩ፣ በጣምም አንፍጠጥ ያስተዛዝባል።” ethiopian unity

ለማጠቃለል ያህል የሚሰራ ጋዜጠኛ፣ ለውጥ ለማምጣት የሚተጋ ፖለቲከኛና የዲሞክራሲ ታጋይ በሂደት ውስጥ ስህተት ሊሰራ ይችላል፣ ከስህተቶች ትምህርት ወስዶ ለሁለተኛ ጊዜ ተመሳሳይ ስህተትን ላለመድገም ጥረት ማድረግ ግን ሊለመድ ይገባል። ነገሮቻችን ሁሉ “ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ” እንዳይሆኑ ሃላፊነት ወስደን ከስህተቶቻችን ለመማር ዝግጁ እንሁን።

Image

(ሁኔ አቢሲኒያዊ ከፒተርቦሮው ዩ.ኬ) :-አቶ ስብሃትን ጠጋ ብለው የሚያውቁት ሰዎች “አቦይ ብላችሁ አትጥሩት። አባታዊ አንደበትና ምግባር የለውም እርሱን አቦይ ማለት ትግራይ የሽማግሌ መሀን እንደሆነች መቁጠር ነው” ይሉታል፡፡

ሰውዬው ስብሐት ነጋ የህወሓትን አመሰራረት ቅድመ ታሪክ ለሚያውቅ ሰው ምን ያህል ተንኮለኛ እና በዘር ልክፍት የተለከፈ እንደሆነ ግልጽ ይሆንለታል፡፡ በ1963 ዓ.ም እንደተመሰረተ የሚነገርለት ማገብት (ማህበር ገስገስቲ ብሔረ ትግራይ) የተመሰረተው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የትግራይ ተወላጅ ተማሪዎች ነበር፡፡ የማህበሩ ተልእኮም የተለያዩ የበጐ አድራጐት ስራዎችን በክረምት ወደ ትግራይ በመሄድ ማከናወን የሚል ነበር፡፡ በሂደት ሙሉ በሙሉ ወደ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በመቀየር ለተሐህት/ህወሓት መመስረት መሰረት ሆነ ለዚህ ዓላማ የማስቀየር ስራ ትልቁን አስተዋፅኦ ካደረጉት መካከል ደግሞ ዛሬ ታሞ የሚማቅቀው ስብሐት ነጋ አንዱ ነው፡፡

ስብሐት ነጋ የህወሀትን መስመር እና ዓላማ መሀንዲስ ከመሆንም አልፎ እስከዛሬ ለብዙ ሰዎች ምስጢር በሆነ መልኩ መለስ ዜናዊንም ወደ ህወሀት ሊቀመንበርነት ብሎም የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስተር ያደረገ እና በህወሀት ክፍፍል ወቅትም ትልቅ ሚና ከነበራቸው ቀደምት የህወሀት ታጋዮች አንዱ ነው፡፡

ለባለፉት 23 ዓመታት የኢትዮጵያን ህዝብ ከጀርባ ሆነው ሲያንቀጠቅጥ የነበረው አይተ ስብሐት ነጋ እርሱም ተራው ደርሶ ቤልጅየም ብራሰልስ በሚገኘው ሴንት ሚካኤል ሆስፒታል Hôpital Saint Michel – (Brussels) መመላስ ከጀመረ 11 ዓመታት እንደሞላው የውስጥ አዋቂዎች ቢገልፁም የበሽታው አይነትና የሰውዬው የጤንነት ሁኔታ እስካሁን ድረስ ከቅርብ ሰዎች ውጪ ሳይወጣ ቀርቷል ሆኖም የህወሀት የውስጥ ሹኩቻን ተከትሎ ሚስጥሮ እያፈተለኩ መውጣታቸውን ቀጥለው ዛሬ ስለ ስብሀት ነጋ ጤንነት በተመለከተ ለዚህ ጽሁፍ ፀሀፊ አፈትላኪ መልዕክት ደርሷል፡፡

ከታማኝ ምንጮች የተገኙት መረጃዎች እንደሚያሳዩት ሰውዬው ማለትም ስብሐት ነጋ brainstem glioma በተባለ የካንሰር አይነት መጠቃቱን ገልፀዋል፡፡ ይህ የካንሰር አይነት በብዛት በህፃናት ላይ የሚታይ ሲሆን በአዋቂዎች ዘንድ ግን በዚህ የካንሰር ዓይነት የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ከ100,000 አንድ እንደሆነ የሳይንስ ማስረጃዎች ያሳያሉ፡፡

Brainstem glioma ስለተባለው የካንሰር አይነት መንስዔ እስካሁን የህክምና ባለሙያዎች ምንም ያሉት ነገር ባይኖርም በካንሰሩ የተጠቃ ሰው ግን ከፍተኛ የሆነ የራስ ህመም፣ ራስን የመቆጣጠር እና የማስመለስ ችግር እንደሚያጋጥመው ያስረዳሉ፡፡

በዚህ ካንሰር ተጠቅተው ወደ ህክምና ከሄዱ ሰዎች መካከል 37% የመኖሪያ እድሜያቸው ቢበዛ ዓንድ ዓመት 20% ያህሉ ሁለት ዓመት 13% ቢበዛ ቢበዛ ከሶስት አመት በላይ በህይወት የመኖር እድላቸው አነስተኛ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

ከህወሀት አፈትልኮ የወጣው መረጃ እንደሚያሳየው ስብሐት ነጋ ባለፉት 11 ዓመታት ቤልጂየም ሲመላለስ የነበረው በዚሁ የካንሰር ምክንያት እንዳልነበረ እና የዚህ አይነት የካንሰር ተጠቂ እንደሆነ የተነገረው ፌብራዋሪ 9 እለተ እሁድ ቀን እንደነበር ጨምረው ገልፀዋል፡፡

የአቶ ስብሐት ነጋን መታመም ተከትሎ በሰውዬው ላይ በየዕለቱ የተለያየ ባህሪ እንደሚመለከቱ ገልፀው በተደጋጋሚ ከተለያዩ ስብሰባዎች ላይ አቋርጠው እየሄዱ እንደሚገኙ አክለው ገልፀዋል፡፡

በጦርነቱ ዘመን የትግራይ ህዝብ እጅግ የከፋ ድርቅና ረሀብ ሲፈራረቅበት፤ ከመሀል አገር የእርዳታ እህል እንዳይደርሰው መንገድ በመዝጋት፤ እነሱ በተቆጣጠሩት አካባቢና ባልተቆጣጠሩትም አካባቢ “እኛ ነን ለህዝባችን ረድኤት ድርጅቶች የሚያቀርቡትን እርዳታ ማደል ያለብን” ብለው የተባበሩት መንግስታትን ግራ አጋብተው ለረሀብተኛው እንዲያከፋፍሉ መድሀኒትና ምግብ ይሰጣቸው የነበሩ ሲሆን ያንን በብዙ ሚሊዮን የሚገመት የእርዳታ እህልና ቁሳቁስ ከአረብ ነጋዴዎች ጋር በመመሳጠር በቀጥታ ባህር እያሻገሩ በመሸጥ፤ በኩንታሎች አሸዋ እየሞሉ ለጋሾችን በማታለል እንዲገዙአቸው በማድረግ፤ በሚሊዮን ዶላር ሲንበሸበሹ፤ የጦር መሳሪያ ሲሸምቱ፤ የትግራይ ህዝብ እንደቅጠል ይረግፍ ነበር። እነሱ በየጫካው ከሰራዊቱ እየተሸሸጉ አረቄ ጠግበው ከውሽሞቻቸው ጋር ከበሮ እየደለቁ እየጨፈሩ ይዳሩ እንደነበር ህወሀትን ጥለው የኮበለሉ የቀድሞ አባላቶች የሚገልፁ ሲሆን ለእነዚህ ሁሉ ግፍ እና በደል መፈፀም ከፍተኛ ሚና የነበራቸው እኚሁ የካንሰር ተጠቂ ነበሩ፡፡

ሞት ፍትሃዊ ነው በቅርቡ እንኳን አፈ ቀላጤ መለስ ዜናዊን ከህወሀት አለማየው አቶምሳን ከኦህዴድ ( ኦህዴድ ብዬ ስጠራው የዋሸው ይመስለኛል) የወሰደ ሲሆን አሁን አፉን ከፍቶ ከስብሐት ነጋ ደጃፍ ደርሷል ስብሀት ነጋም ሞትን ወደ ቤቱ ላለማስገባት ከአዲስ አበባ ወደ ብራሰልስ በየዕለቱ እየተመላለሰ ይገኛል ግና ሞትን ሸሽቶ እስከመቼ ሊደበቅ እስከ አንድ ወር ወይስ?

አፈንዲ ሙተቂ
———-
ኤርትራ ዛሬ ራሷን የቻለች ሀገር ናት፡፡ ትናንት ግን የኛው አካል ነበረች፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሤ ብልጥ የሆኑ መስሎአቸው ለሁላችንም አስፈላጊ የነበረውን የፌዴሬሽን ፎርሙላ ሰረዙትና ህዝቡን አስቀየሙት፡፡ ደርግ ደግሞ የራሳችንን ህዝብ እንደ ባዕድ እየቆጠረ በመትረየስ አጨደው፡፡ በታንክ ደመሰሰው፡፡ በዚህም የተነሳ ወጣቱ “አደይ ኤሪቲሪያ”ን እየዘመረ ወደ ባርካና ሳህል ነጎደ፡፡ ራሱን አደራጅቶ ጀብሃና ሻዕቢያ ሆኖ መጣ፡፡ ውጤቱም 1983 ላይ ታየ፡፡

የደርግና የኃይለ ሥላሤ መንግስታት ያደረጓቸው ነገሮች ሲገርሙን በጣም ግራ የሚያጋባው ሶስተኛው መንግሥታችን መጣ፡፡ ይህ የኛ መንግሥት “የተበላሸውን ሁሉ አስተካክለን አብረን መኖር እንችላለን” ብሎ መከራከር ሲገባው ጭራሹኑ “ኤርትራ ካልተገነጠለች ኢትዮጵያ ሰላም አታገኝም” ባይ ሆኖ ተገኘ፡፡ ክፍለ ሀገሩ ወደዚያ ከሄደ በኋላም መንግሥቱ ከሚከተለው ግልጽነት የጎደለው አሰራር የተነሳ በ1990 ዓ.ል. ሺዎችን ያረገፈ ግዙፍ ጦርነት ተቀሰቀሰ፡፡ ከአንድ ምንጭ የተቀዱ ህዝቦች ተጋደሉ፡፡ እነሆ ዛሬም ድረስ ነገሩ ሳይለይለት በጨለማ ውስጥ ነው ያለነው፡፡

እኛ ግን ተስፋ አንቆርጥም! በአያያዝ ጉድለት የተለየንን ወገናችንን መመለስ እንፈልጋለን፡፡ ህዝቡ ለጊዜው ሪፈረንደም አድርጎ ነጻነቱን ማወጁን ብንደግፍለትም አንድ ቀን ተቀራርበን በጋራ ስለመስራት እንወያይ ይሆናል ብለን እናልማለን፡፡ የኛ ልጆች ደግሞ በኮንፌዴሬሽን ስለመስራት ያስቡ ይሆናል፡፡ የልጅ ልጆቻችን በፈቃደኝነት ስለመዋሃድ ያስቡ ይሆናል፡፡ በዚያን ጊዜም አሁን የምንመኘው በአንድነት ውብ የመሆን ሚስጢራችን ይመለስልናል ብለን እናልማለን፡፡ ምን ይታወቃል?

ወገኖቼ ደጉን ነው የተመኘሁት፡፡ በቅን ልቦና በርትተን ከጸለይንና ከኛ የሚጠበቀውን ካደረግን ሁሉንም የሚችለው ፈጣሪ ህልማችንን እውነት ያደርግልናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
——-
ምን እንደጣለብኝ እንጃ! ያንን ምድር እጅግ ሲበዛ እወደዋለሁ፡፡ እኔ ለተወለድኩበትና አብዛኛውን ዘመኔን ለጨረስኩበት የምስራቅ ኢትዮጵያ ክልል ጎረቤት ከሆነችው ሶማሊያ ይልቅ በ1600 ኪ.ሜ. የምትርቀው አስመራ ናት የምትናፍቀኝ፡፡ ስለሶማሊያ የተጻፈ መጽሐፍ ማንበብ ብዙም አይማርከኝም፡፡ ስለ ኤርትራ የተጻፈ መጽሐፍ ካጋጠመኝ ግን ሳላየው አላልፍም (ይህ ግን ሶማሊያን ከመጥላት እንደማይቆጠርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ)፡፡

ታዲያ በርካቶቻችሁም እንደኔው ትመስሉኛላችሁ፡፡ ለምሳሌ ከ1970ዎቹ ጀምሮ ሲታተም የቆየው የቤኒ አምሩን ወጣት የሚያሳየው ፖስተር ዛሬም ድረስ ከኛ ጋር ተሳስሮ ነው ያለው፡፡ አሁንም ድረስ በበርካታ ስፍራዎች ተለጥፎ አይቼዋለሁ፡፡ በፌስቡክም እርሱን እንደ ፕሮፋይል ፒክቸር የሚጠቀም ኢትዮጵያዊ ሞልቷል፡፡ በሌላ በኩል የኤርትራን ሙዚቃ የሚያዳምጡ ሰዎች በሽ ናቸው፡፡ ደራሲ መሐመድ ሳልማን መቐለ ሄዶ ያየው ነገር ቢያስገርመው “በኤርትራ ሙዚቃ የምትጨፍር ከተማ” የሚል አስደናቂ ወግ ጽፎ እውነቱን አስረድቶናል፡፡ መንግሥታት ቢጣሉ እንኳ ህዝቦች ምንጊዜም እንደሚነፋፈቁ ከዚህ በላይ የሚያስረዳ ዋቢ ያለ አይመስለኝም፡፡
——–
ማርታ ሀይሉን አስታወሳችኋት? አዎን! ማርታን “ብራ… ነው… ብራ ነው”፤ “አዘዞ”፤ “ሎጋ ..ና እናውጋ” በተሰኙት ዘፈኖቿ እናውቃታለን፡፡ ከማርታ ዘፈኖች ዘወትር ቀልቤን ይገዛ የነበረው ግን የትግርኛ ዜማዋ ነው፡፡ አዝማቹ እንዲህ ይመስለኛል፡፡

ካብ አስመራ ድንገት ርእዮ
ምጽዋ ገባሁ ልበይ ሕብዮ

እንተርጉመው እንዴ?… ግድ የለም ማርታ ራሷ እንዲህ እያለች በአማርኛ ተርጉማዋለች፡፡

“ከአስመራ ድንገት አይቼው
ምጽዋ ገባሁ ልቤን ሰጥቼው”፡፡

አዎን! ትናንት የኛ ናት ስንላት ለነበረችው ኤርትራ ነው እንዲህ የዘመርንላት፡፡ ዛሬም ብንዘምርላት እንከበራለን እንጂ አንወቀስም፡፡ ምክንያቱም በመንግሥት ደረጃ ነው የተለያየነው፡፡ ሁለት ፓስፖርት እንዲኖረን ነው የተደረግነው፡፡ ሁለታችንም ግን አንድ ህዝቦች ነን፡፡ በደምም ሆነ በባህል በጣም የተዋሃድን የአንድ መሬት ብቃዮች ነን፡፡ ሁለታችንም የተዋብን የሴምና የኩሽ ህዝቦች ውቅር ነን፡፡ እንደኛ የሚያምር ህዝብ በትኛውም ዓለም የለም፡፡ የጀበና ቡና፣ ዶሮ ወጥ፣ ድፎ ዳቦ፣ የስጋ ፍትፍት፣ አምባሻ፣ ወዘተ…. ሁለታችን ዘንድ ብቻ ነው ያለው፡፡
—–
በርግጥ እላችኋለሁ፡፡ በምንባብና በወሬ እንጂ በአካል የማላውቃት ኤርትራ ትናፍቀኛለች! ያ በታሪክ ምዕራፎች “ምድሪ ባህረ ነጋሽ” እየተባለ ሲጠራ የኖረው ጀግና መሬትና ህዝብ ይናፍቀኛል፡፡ ያ የሰሜኑ በረኛ እያልን እንመካበት የነበረው ህዝባችን ይናፍቃል፡፡
እውነትም ኤርትራ ! የዳማት ታሪክ ውቅር! የመጠራ አብያተ መንግሥታት ከርስ! የሀውልቲ ፍርስራሾች ቀብር! የአዱሊስና የዙላ ወደቦች መዘክር! የሱዋኪምና የዳህላክ ሱልጣኖች ደብር!
ኤርትራ የአብረሃ ደቦጭ ሀገር! የሞገሥ አስገዶም ሀገር! የዘርዓይ ደረስ ሀገር! የሎሬንዞ ታዕዛዝ ሀገር! የደጃች ሀረጎት ሀገር! በአይበገሬ ጀግንነታቸው ድፍን አፍሪቃን ያኮሩ አርበኞች የበቀሉበት ምድር!
ኤርትራ የበረከት መንግሥተ አብ ሀገር! የአብረሃም አፈወርቂ ሀገር! የአሕመድ ሼኽ ሀገር! የሄለን መለስ ሀገር! የየማነ ባሪያው ሀገር! የሄለን ጳውሎስ ሀገር! በስርቅርቅ ድምጻቸው የሰውን ልብ እየሰረሰሩ የመግባት ሀይል ያላቸው የጥበብ ከዋክብት የወጡበት መንደር!
ኤርትራ የፊያሜታ ጊላይ ሀገር! የስዕላይ በራኺ ሀገር! የኦቦይ ተኽሌ ሀገር! የተክላይ ዘድንግል ሀገር! የሆቴል ፓራዲዞ ሀገር! የዕቁባይ ሲላ ሀገር! የምንወደው ደራሲያችን በዓሉ ግርማ በ“ኦሮማይ” መጽሐፉ እንደ ፊልም ግልጥልጥ አድርጎ እየተረከልን ዝንተ-ዓለም እንድንወዳት ያደረገን የቀይ ኮከብ ትዝታ ወመዘክር!
ኤርትራ የፊዮሪ ሀገር! የሳባ ሀገር! የማርቲና ሀገር! የብርኽቲ ሀገር! ፊያሜታ ጊላይን የመሳሰሉ “ሽኮሪናዎች”ን ያበቀለች ውብ የውቦች እመቤት!
—–
ኤርትራን ስንጠራ በቅድሚያ ወደ አዕምሮአችን የምትመጣው አስመራ ናት፡፡ የአስመራ ናፍቆት ይገድላል፡፡ አስመሪና፣ አስመሪቲ፣ አቲ ጽብቕቲ!…
ውይ ስታምር! “ቀሽቲ” እኮ ናት፡፡ ያኔ በልጅ አዕምሮአችን በዘምባባ ጥላዋ ተሸክፋ በፖስትካርድ ስትቀርብልን “የኛ ውቢት” እያልን እንመጻደቅባት ነበር፡፡ እንቆቅልሽ ስንጫወትና መልሱ ጠፍቶን “ሀገር ስጠኝ” ስንባል እርሷን ለመስጠት እንሰስት ነበር፡፡ ጠያቂውም የዋዘ ስላልሆነ “አስመራ” ካላልነው ለጠየቀን ጥያቄ ትክክለኛውን መልስ አይነግረንም ነበር፡፡ ከማናውቃቸው “ዋሽንግተንና” ሮማ አስመራ ነበር የምትበልጥብን፡፡ በትምህርት ቤት መዝሙራችንም እንዲህ እንል ነበር፡፡
ኦኬ ኦኬ ኦኬ ስራ
ሰላም ሰላም ወደ አስመራ
አዲስ አስተማሪ ከጃፓን የመጣ
ማስተማሩን ትቶ በቦክስ የሚማታ
አናግረኝና አናግርሃለሁ
በአሜሪካ ሽጉጥ አዳፍንሃለሁ፡፡

ግጥሙ “አንታራም” የሚሉት የህጻናት ጨዋታ ዓይነት ነው፡፡ ነገር ግን አስመራ ከልባችን እንዳትጠፋ አድርጓል፡፡ ዛሬም በልባችን ነግሳለች አስመሪና!
—-
አስመሪና! እንተይ ሽኮሪና! ሰሜናይት ጽብቕቲ! በዓሉ ግርማ ላንቺ ክብር የጻፈው ትዝ ይልሻል? እስቲ እናስታውሰው!

አስመሪና አስመራዬ
ካብ ሐንቲ ንግሥቲ ይበልፅ መልክእኪ
አማአድዬ ክርእየኪ ከሎኹ ኽአ
አብ ኢደይ ዘሎ ነገር ይወድቕ፡፡
——
ጸጸራት፤ ፎርቶ፣ ሐዝሐዝ፣ አርበእተ አስመራ፣ እምባጋሊያኖ፣ ኮምቢሽታቶ፣ አዲጓእዳድ፣ ቃኘው፣ ማይተመናይ፣ ሰምበላይ፣ ጎዳይፍ፣ ገጀረት፣ ወዘተ…በጽሑፍ የማውቃቸው የአስመራ ሰፈሮች ናቸው፡፡ አንድ ቀን በሆነልኝና ባየኋቸው እያልኩ አልማሁ፡፡ እነዚህ አስገራሚ የአስመሪና ሰፈሮች ብዙ ባለታሪኮችን አብቅለዋል፡፡ ብዙዎች ገድላቸው እየተደጋገመ ሲነገርላቸው እሰማለሁ፤ አነባለሁ፡፡ ለኛ ቅርብ የነበረ አንድ ውድ ልጅ እየተረሳ በመሆኑ ግን አዝኛለሁ፡፡

አማኑኤል እያሱ ይባላል! አስታወሳችሁት አይደል? አዎን! አማኑኤል በኛ ዕድሜ ዘመን ኢትዮጵያ ዋንጫ መብላት እንደምትችል ያስመሰከረው የታላቁ የ1980 የእግር ኳስ ቡድናችን ቋሚ ተሰላፊ ነበረ፡፡ የማሊያ ቁጥሩ 2 ይመስለኛል፡፡ አማኑኤል የያኔው ቡድናችን ባደረጋቸው ሁሉም ጨዋታዎች ተሰልፏል፡፡ ቡድኑ ዋንጫውን ሲበላም ከጓደኞቹ ጋር ቤተመንግሥት ድረስ ተጋብዞ ተሸልሟል፡፡ አማኑኤልን ያስገኘው ከዚያ ዘመን ዝነኛ ቡድኖቻችን መካከል አንዱ የነበረው የኤርትራ ጫማ ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን የኤርትራ አንደኛ ዲቪዚዮን ዋንጫን በተደጋጋሚ ያሸነፈ ነው፡፡

አማኑኤል እያሱ በኢትዮጵያ ትቅደም አንደኛ ደረጃ ዋንጫም ለኤርትራ ክፍለ ሀገር ምርጥ ቡድንም ተሰልፎ ተጫውቷል፡፡ ባልሳሳት የ1981 የኢትዮጵያ ዋንጫን ያሸነፈው እነ አማኑኤል የነበሩበት የኤርትራ ክፍለ ሀገር ቡድን ነው፡፡ የአማኑኤል እያሱን ወሬ ለመጨረሻ ጊዜ ያነበብኩት በ1988 ለወዳጅነት ጨዋታ አዲስ አበባ መምጣቱን በማስመልከት በርካታ የግል ጋዜጦች ቃለ-መጠይቅ ባደረጉለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ መረጃው የለኝም፡፡ እስቲ የአስመራ ልጆች ወሬው ካላችሁ ስለአማኑኤል እያሱ አንድ ነገር በሉን፡፡
—–
ወደ ምዕራብ ኤርትራ ተሻግረናል! ባርካና ጋሽ የሚባሉት የኤርትራ ቆላዎች እዚህ ነው ያሉት፡፡ አቆርዳት፣ ተሰነይ፣ አሊጊደር፣ ባሬንቱ የተሰኙት ከተሞችም በቆላው ውስጥ ተዘርግተዋል፡፡ ኩናማ፣ ናራ እና ቤጃ የተሰኙት ብሄረሰቦች እዚህ ነው የሚኖሩት፡፡ የአካባቢው ዋነኛው ህዝብ ግን ለኛ በጣም ቅርብ ሆኖ ዓመታትን ያስቆጠረውን ሳቂታውን የቤኒ አምር ወጣት ያስገኘው የትግረ ህዝብ ነው፡፡

የትግረ ህዝብ በውስጡ በርካታ ጎሳዎች አሉት፡፡ ከሁሉም የሚበረክተው ግን የቤኒአምር ጎሳ ነው፡፡ ህዝቡ የሚነጋገርበት የትግረ ቋንቋ ከሴማዊ ቤተሰብ ነው የሚመደበው፡፡ ለዚህ ቋንቋ በጣም የሚቀርበው በደጋው ኤርትራና በኛዋ የትግራይ ክልል የሚነገረው ትግርኛ ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ቋንቋዎች ከጥንታዊው የግዕዝ ቋንቋ ነው የተወለዱት፡፡ የትግረ ቋንቋ ከኤርትራ ሌላ በሱዳንም (ከሰላ አካባቢ) በስፋት ይነገራል፡፡

ትግረና ትግርኛ በጣም ከመመሳሰላቸው የተነሳ እንግዳ ለሆነ ሰው አንድ ዓይነት ቋንቋዎች ሊመስሉት ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም ለትግርኛ ተናጋሪዎች የትግረ ቋንቋን መልመድ በጣም ቀላል ነው ይባላል፡፡ የትግረ ተናጋሪም ትግርኛን በቶሎ መልመድ ይቀለዋል፡፡ በመሆኑም በዛሬዋ ኤርትራ ከግማሽ በላይ የሚሆነው ህዝብ ሁለቱንም ቋንቋዎች መናገር ይችላል፡፡

ምዕራባዊው ቆላ ኤርትራዊያን በጣም የሚያደንቋቸውን እንደ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ፣ ሙሐመድ ኢድሪስ እና ኢድሪስ ገላውዴዎስን ያፈራ መሬት ነው፡፡ በዚህ ሰሞኑን ልቤን ያሸፈተው የትግረ ልጅ ግን “አሕመድ ሼክ” ነው፡፡ አሕመድ ሼክን አወቃችሁት አይደል? አዎን! “ባቡሬይ”፣ “ኢላ ሰርጎ” ወዘተ.. እያለ በማይጠገበው የትግረ ምት የሚያዜመው ተወዳጅ ድምጻዊ ነው፡፡ አንድ ኤርትራዊ ወዳጃችን “ኤላ ሰርጎ”ን ሲፈታልን `ከጀርባው ፌሎሶፊ አለው” ነው ያለኝ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡

የትግረ ሴት ለምትወደው አንድ ሰው (ለባሏ) እንጂ ለማንም ጸጉሯን አትገልጠውም፡፡ ስለዚህ ጉብሊቷን ልጅ የወደደው አሕመድ ሼክ በተዋቡ ግጥሞች እያወደሳት ዘፈነላትና ፍቅሩ ልቧ ውስጥ ዘልቆ መግባቱን ለማረጋገጥ ጸጉሯን ማየት ጀመረ፡፡ እርሷም ግጥሞቹን ከሰማችለት በኋላ ጸጉሯን ገልጣ አሳየችው፡፡ ድል አድራጊው ወዲ ሼክም ይዟት በረረ፡፡ ኤላ ሰርጎ! ኤላ ሰርጎ” እያለ ነጎደ!
——
ሰሜን ኤርትራ!
ተወዳጇ የከረን ከተማ እዚህ ነው ያለችው! የሀረርጌዋ የድሬ ዳዋ ከተማ መንትያ እህት የምትመስለው ውቢቷ የሰሜን ፈርጥ! በቪዲዮ አይቻት ውበቷን አደነቅኩላት! አበቦቹ! ቤቶቹ! መንገዶቹ ሁሉም ውብ ናቸው፡፡ ከትግራይ የተገኘው ዝነኛው ብርሃነ ሃይለ አንድ ላይ በነበርነት ዘመን ለከረኗ ጉብል እንዲህ ብሎላታል፡፡

ሸው በሊ ብለነይ ብለነይ
ዝለሊ ብለነይ ብለነይ
አሊሊ ብለነይ ብለነይ
አቲ ጓል ከረነይ ብለነይ

አዎን! ቢለን ከከረን ከተማ ጋር ስሙ የሚጠቀስ ብሄረሰብ ነው፡፡ ቋንቋው ከኛው የአገው ቋንቋ ጋር አንድ ዐይነት ነው፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ነው አንባቢ ሊመራመር የሚገባው፡፡ በወሎና በጎጃም የሚኖረው አገው ምን ሊያደርግ እዚያ ሄደ?… መቼ ነው እዚያ የሄደው?… መላምት ከመዘብዘብ በስተቀር ማንም ሰው ይህንን እንቆቅልሽ በሚያመረቃ ሁኔታ ሊፈታው አልቻለም፡፡ ኤርትራና እኛ አንድ ነን የሚያሰኘኝ እንዲህ ዓይነት ተጨባጭ ማስረጃ ስላለን ነው፡፡

ቢለን ውብ ባህል ያለው ህዝብ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ሴቶቹ ካገቡ በኋላ ጸጉራቸውን መሰተር ግድ ነው፡፡ ህዝቡ የቢለን ቋንቋ ተናጋሪ ቢሆንም የትግረ ቋንቋንም ይጠቀማል፡፡ ትግርኛም በስፋት ይነገራል፡፡ እጅግ ታዋቂ የሆነው የቢለን ተወላጅ “ዑመር እዛዝ” ነው፡፡ የጀብሃ ጦር ከመፍረክረኩ በፊት የሁለተኛው ዞን አዛዥ እንደነበረ ከዚህ በፊት ጽፌ ነበር፡፡

ከከረን ሽቅብ ወደ ሰሜን ስናመራ ታሪካዊቷ አፋቤት አለች፡፡ ጄኔራል ታሪኩ አይኔ የሚመራው ናደው እዝ እዚህ ነበር የሰፈረው፡፡ የቀይ ኮከብ ዘመቻ ዋና አምባም ይህ ነበር፡፡ ከአፋቤት ወደ ሰሜን ስንበር ንዳዳማውና አስቸጋሪው የሳህል መሬት አለ፡፡ በዓሉ ግርማ እንደተረከልን ከሆነ ሳህል ማለት እሳት ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ይኖሩበታል፡፡ ከብቶች ይሰማሩበታል፡፡ ተክልም ይበቅልበታል፡፡ እዚህ አካባቢ በብዛት የሚኖረው ህዝብ “ረሺዳ” ይባላል (አንዳንዶች “ራሻይዳ” ይሉታል፤ ስህተት ነው፤ ትክክለኛው አጠራር “ረሺዳ” ነው)፡፡

የ“ረሺዳ” ህዝብ ከሌላው የኤርትራ ህዝብ የሚለይበት በርካታ ነገሮች አሉት፡፡ ለምሳሌ ይህ ህዝብ ከሳዑዲ ዐረቢያ ተነስቶ ወደ ኤርትራ የገባው በቅርብ ዘመን (በ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ) ነው፡፡ በዚያ ወቅት የአሁኗ ሳዑዲ ዐረቢያ አልነበረችም፡፡ ሀገሩ ሁሉ በጎሳዎች የተከፋፈለ በረሃማ ምድር ነበር፡፡ ከነዚህ ጎሳዎች አንዱ አል-ረሺድ ይባላል፡፡ ይህ የአል-ረሺድ ህዝብ የአካባቢው የበላይ እንዲሆን በኦቶማን ቱርክ ተወሰነ፡፡ አብዛኛው ህዝብም ለነርሱ አደረ፡፡ “አል-ሱዑድ” የሚባለው ቤተሰብ ግን “አሻፈረኝ” አለ፡፡ “ራሴ በረሃውን ጠቅልዬ መግዛት ስችል ለምን በአል-ረሺድ ጎሳ የበላይነት አድራለሁ” በማለት አንገራገረ፡፡ በሁለቱ መካከል ጠብ ተነሳ፡፡ በመጀመሪያው ላይ የአል-ረሺድ ጎሳ አሸነፈ፡፡ አል-ሱዑዲዎች ወደ ኢራቅ ሸሹ፡፡

ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን የአል-ሱዑድ ቤተሰብ በእንግሊዞች ደጋፊነት ራሱን አጠናክሮ መጣ፡፡ በአል-ረሺድ ጎሳ ላይም ድልን ተቀዳጀ፡፡ በዚህም የተነሳ የዐረቢያ በረሃ ለአል-ረሺድ ጎሳ አባላት ሲኦል ሆነ፡፡ ረሺዳዎች እየተያዙ በጅምላ ታረዱ፡፡ ንብረታቸው ተዘረፈ፡፡ በፊት ይረዳቸው የነበረው የቱርኮች መንግሥት በራሱ ችግር በመወጠሩ ምንም ሊያደርግላቸው አልቻለም፡፡ በመሆኑም ከእልቂቱ ለመዳን ሲሉ ባህር እያቋረጡ ወደ አፍሪቃ ምድር ተሰደዱ፡፡ በሱዳንና በኤርትራ መኖሪያቸውን ቀለሱ፡፡

እንግዲህ ረሺዳዎች ከዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሸሽ ወደ ኤርትራ የመጡ ተፈናቃዮች ናቸው ማለት ነው፡፡ በኤርትራ ውስጥ ንጹህ የዐረብ ዝሪያ የሚባሉት እነርሱ ናቸው፡፡ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸውም ዐረብኛ ነው፡፡ በረሺዳ ባህል መሰረት ለአካለ መጠን የደረሰች ማንኛዋም ሴት ፊቷንም ሆነ ጸጉሯን መሸፈን ግዴታዋ ነው፡፡ በዓሉ ግርማ በኦሮማይ ውስጥ ሲተርክልን “ማንኛውም የረሺዳ ባል የሚስቱን ፊት ገልጦ የሚያይበትን ሰው አይፈልግም” በማለት የተናገረውም የባህላቸው አንድ አካል ነው፡፡
—————–

ታላላቅ ግድቦችን በመሥራት ላይ የሚገኙ ታዳጊ አገራት ለከፍተኛ ችግር መጋለጣቸው ተነገረ፡፡ በጉዳዩ ላይ ጥናት ያደረገው የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ባወጣው ዘገባ መሠረት አገራቱ ለከፍተኛ ዕዳ እና ከዚያ ጋር ተዛማጅ ለሆኑ ችግሮች የሚጋለጡ መሆናቸውን ፋይናንሺያል ታይምስ ጥናቱን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡ “ለሕዝባችሁ የምታስቡ ከሆነ ገንዘቡን ለሌላ ተግባር አውሉት” በማለት ምክርም ሰጥቶዋል፡፡

እኤአ ከ1934ዓም ጀምሮ በ65 አገራት የተገነቡ 245 ግድቦችን በማካተት የተደረገው በዓይነቱ ለየት ያለው አጠቃላይ ጥናት በቅርቡ እየተገነቡ ያሉትን ታላቅ ግድቦችንም ያካተተ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ካለው የግልገል ጊቤ ሦስት ግድብ ጀምሮ እስከ ብራዚሉ የአማዞን ቤሎ ሞንቴ የግድብ ፕሮጀክቶችን የሚገነቡት ታዳሽ ኃይልን አጠቃቀም ለማጎልበት እና የኤሌክትሪክ አቅርቦትን ለመጨመር በሚል እንደሆነ የጠቀሰው ጥናታዊ ዘገባ ግንባታው በርካታዎችን ከመኖሪያቸው እንዲፈናቀሉ የሚያደርግና ለብዝሃ ህይወት አደጋ እንዲጋለጡ የሚያደርግ መሆኑን ጠቁሟል፡፡

እንደነዚህ ዓይነቱን የግድብ ሥራ የሚቃወሙ ቡድኖች እንደሚሉት የታላላቅ ግድቦች የኮንስትራክሽን ወጪ ሲጀመር ከታሰበው በጀት በአማካይ ከ90 በመቶ በላይ ተጨማሪ ወጪ የሚያስከትል እንዲሁም ከአስር ግድቦች ስምንቱ ከተወሰነላቸው የመጠናቀቂያ ጊዜ እንደሚያልፉ ይናገራሉ፡፡ በመሆኑን በኢትዮጵያና በብራዚል የሚገነቡት ግድቦች የፓኪስታንንና የምያንማርን (በርማ) ጨምሮ “ከፍተኛ ወጪ እንዲሁም ከመመጠናቀቂያ ጊዜያቸው በማለፍ የአገራቱን የኢኮኖሚ ገጽታ ችግር ውስጥ” እንደሚከቱ ዘገባው ያስረዳል፡፡

ጥናቱን ያቀረቡት ምሁራን እንደሚሉት ግድብ መሥራት አስፈላጊና እነርሱም በዚህ ጉዳይ ላይ ተቃዋሚ አለመሆናቸውን በአጽዕኖት ተናግረዋል፡፡ ችግሩ ያለው ታዳጊ አገራቱ ካላቸው የኢኮኖሚ ሁኔታ አኳያ በእንደዚህ ዓይነት የታላላቅ ግድብ ሥራ ላይ መጠመዳቸው ወደፊት ግድቦቹ በሥራ ላይ ሲውሉ ከሚጠይቁት ከፍተኛ ወጪና አገራቱ ግድቦቹን ለማንቀሳቀስ ከሚጠፈለግባቸው ከፍተኛ የፋይናንስ ጥያቄና ብቃት ማነስ አኳያ ሁኔታው እጅግ አሳሳቢ መሆኑን በመዘርዘር አስረድተዋል፡፡ “በመሆኑም” ይላሉ ከምሁራኖቹ አንዱ “በመሆኑም ይህንን ሁሉ ሁኔታ አንድ ላይ ስንወስደው ግድቦቹን መገንባት ስሜት የሚሰጥ አይደለም፡፡”

እንዲህ ያለው መረጃና ማስጠንቀቂያ ይፋ ቢሆንም የግድቦቹን መሠራት የሚደግፉ ወገኖች ቀድሞ የተሠሩ ስህተቶች እንዳይደገሙ አድርገን ነው የምንገነባው በማለት ለሚቀርበው ማስረጃ መከላከያ ይሰጣሉ፡፡ ሆኖም የኦክስፎር ዩኒቨርሲቲ ዘገባ የበርካታ ዓመታት መረጃ በመውሰድ ያወጣው ዘገባ ላይ እንዳመለከተው የግድቦቹን ሥራ ለማጠናቀቅ፣ ከተሰሩም በኋላ ለጥገናና ግድቦቹ በሥራ ላይ እንዲቆዩ ለማካሄድ የሚወጣው ወጪ ባለፉት በርካታ ዓመታት እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ እንዳልመጣ ያስረዳል፡፡ በጥናቱ ላይ የተሳተፉ ሌላው ምሁር ሲናገሩ “እነዚህ ኢኮኖሚያችን እያደገ ነው የሚሉ አገራት በእርግጥ ለዜጎቻቸው ዋስትና ግድ የሚላቸው ከሆነ ገንዘባቸውን ከታላላቅ ግድብ ሥራ ይልቅ በሌላ (ሰብዓዊ) ተግባር ላይ ቢያውሉት ይሻላል” ብለዋል፡፡

ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ድርጅት የኦሞ ወንዝን ተከትሎ በሚገነባው ግድብ ላይ ስለተፈናቀሉት ዜጎች በቅርቡ ባወጣው በሳተላይት ፎቶ በተደገፈ ማስረጃ መሠረት በኢትዮጵያና በኬኒያ የኦሞን ወንዝ ተከትለው የሚኖሩ እስከ ግማሽ ሚሊዮን የሚደርሱ የአካባቢው ነዋሪዎች በግድቡ ሥራ ምክንያት የመኖር ኅልውናቸው ያከተመ መሆኑን ዘግቦ ነበር፡፡ ሰሞኑን የኢህአዴግ ባለሥልጣናት (ከግብርና ሚ/ር) በኢህአዴግ ፓርላማ ሲጠየቁ በሰጡት ቃል አንዳችም የተፈናቀለ ሰው የለም በማለት የመለሱ ሲሆን በተደጋጋሚ ማስረጃ ተደግፎ የሚወጣውን መረጃ አጣጥለውታል፡፡
Image
(ፎቶ: AP)

goolgul

የኢሕአዴግ አባል ፓርቲዎች በዶ/ር ደብረጺሆን ፍቃድ ካልሆነ ምንም አይነት ውሳኔ መስጠት አይችሉም::

የደህንነት ሹሙ አቶ ጌታቸው አሰፋና ባለስልጣኖቻቸው በሙስና እና በዘረፋ ላይ ተሰማርተዋል::
የፍርድ ቤቶች እና የተቃዋሚ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴ ማኮላሸት ለአለቃ ጸጋዬ በርሄ ተሰቷቸዋል::
የጦር ሰራዊቱን በተጠንቀቅ የሚከታተሉ ወታደራዊ ደህንነቶች ተደራጅተው በየእዙ ተበትነዋል::

ምንሊክ ሳልሳዊ በመከላከያ ሰራዊት የሕወሓት መኮንኖች ስር የሰደደው የሙስና እና የዘረፋ አድራጎት በደህንነት መስሪያ ቤት ውስጥም ከሹሙ ከአቶ ጌታቸው እና ከባለስልጣኖቻቸው ጀምሮ እስከ ገራፊዎች ድረስ መንሰራፋቱን ውስጥ አዋቂ ምንጮች ገልጸዋል:: እንደውስጥ አዋቂ ምንጮቹ መረጃ ከሆነ የደህንነት ባለስልጣኖቹ የተዘፈቁበት የሙስና ተግባር በተጨማሪ ዘረፋን እና ሴት መድፈርን እንዲሁም የቡድን ወንጀሎችን ያካተተ መሆኑ ተጠቁሟል::በተለያዩ ከተሞች የሚገኙ ባለሃብቶችን በማስፈራራት ከፍርድ ቤት ትእዛዝ ውጪ በማሰር እንዲሁም የሙስና ወንጀል ተገኝቶብሃል ይህን ያህል ገንዘብ አምጣ ካላመጣህ እንገድልሃለን እስከማለት በከመድረሳቸውም በተጨማሪ ይህንን ጉዳይ ለፖሊስ የጠቆመ ባለሃብት በማፈን ንብረቱ ባማገድ እና በተለያዩ ስልቶች የተጠየቀውን ገንዘብ እንዲሰጥ በማስገደድ ላይ መሆናቸውን ምንጮቹ ጠቁመዋል::

ከዚህ ቀደም በሙስና የተከሰሱ የስርኣቱ ባለስልጣናትን ተገን በማደርግ በአዲስ አበባ ውስጥ የሚገኙ ባለሃብቶችን በመከታተል እና ደህንነት ቢሮ ድረስ በመውሰድ በሙስና ከታሰረው ስም እየተጠቀሰ … ከሚባል ባለስልጣን ጋር ግንኙነት አለህ ማስረጃ ተገኝቶብሃል በማለት በፈጠራ ወንጀል ባለሃብቱን በመዝረፍ ስራ ላይ ተሰማርተው የነበረ እና እንዲሁም የአዲስ አበባን ቆነጃጅት ቢሯቸው ድረስ በግብረአበሮቻቸው አፋኝነት እና አስገዳጅነት በመውሰድ ካለፍላጎታቸው አስገድደው በመድፈር ላይ ናቸው ያሉት ምንጮቹ ተራ የደህንነት አባላት ለዚሁ ተልእኮ ተሰማርተው የሚሰሩት ምንም አይነት ወንጀል በቡድን ሲፈጽሙ የሚጠይቃቸው አለመኖሩን የሕዝቡን በደል የከፋ አድርጎታል::ምንሊክ ሳልሳዊ

ኢትዮጵያውያን በሕወሓቱ የደህንነት መዋቅር የሚመራ የሽብር ተግባራትን አጥብቆ ስለሚፈራ እና በየጊዜው በሕወሓት ደህንነቶች መሪነት የሚወሰዱ እርምጃዎች በሃገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ስጋትን በመፍጠራቸው በየእስር ቤቱ የሚካሄዱ ሕገወጥ ጸረ ፍትህ ተግባራት እና የሰብኣዊ መብት ጥሰቶች የኢትዮጵያውያን የቀን ተቀን አጀንዳ ሆነው መምጣታቸው ገዢው ፓርቲ ሕዝቡን ምን ያህል እንዳሸበረ ይጠቁማል ሲሉ ምንጮሹ አክለው ገልጸዋል::

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሕወሓትን ሳይጨምር ብኣዴን ኦሕዴድ ደኢሕዴግ እና አጋል የክልል ጎሳ ፓርቲዎች ከአቶ ደብረጺሆን በሚወርድ ትእዛዝ ካልሆነ በስተቀር ምንም አይነት እርምጃ በፍቃዳቸው መፈጸም እንደማይችሉ ተነግሯቸዋል:: በቅርቡ የአቶ አለማየሁ አቶምሳን ሞት ተከትሎ አፈጻጸሙ በዶ/ር ደብረጺሆን መልካም ፍቃድ እንደሆነ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር የተባለው የኦሕዴድ ሙክታር ከድር አቶ አለማየሁ ደክመው እያየ እና እያወቀ ሆስፒታል እንዲሄዱ አስቸኳይ ትብብር እንዲደረግ ወይዘሮ አስቴር ማሞ ስትጠይቀው ለዶ/ር ደብረጺሆን ነግረሽ አስፈቅጂ በማለት ሕወሓት በኦሕዴድ አናት ላይ ምን ያህል እየሸና እንዳለ እንዲሁም በሞራላቸው አመራሮቹ እንዳይራመዱ እያደረገ እንዳለ ፍንትው አድርጎ ያሳየ ነው:: ማንኛውም የኢሕኣዴግ አባል እና አጋር ድርጅት በድርጅቱ ሊቀመንበር ወይንም ምክትል አማካኝነት በቅድሚያ ለዶ/ር ደብረጺሆን ሪፖርት ማድረግ እና ሁኔታው ታይቶ ፈቃድ እና ውሳነ ካልተሰጠው በስተቀር መፈጸም እንደማይችል ትእዛ መተላለፉ ሲታወቅ በአዲስ አበባ እና በክልል ያለው የፍርድ ቤቶች እና የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ በአለቃ ጸጋይ በርኸ ስር ክትትል እየተደረገ እርምጃ የሚወሰድበት መሆኑ ሲታውቅ የጦር ሰራዊቱን በተመለከት በተዋረድ የሚያስተዳድሩ የወታደራዊ ደህንነት የሕወሓት መኮንኖች ተደራጅተው በየእዙ መመደባቸው ታውቋል:: ምንሊክ ሳልሳዊ

Image

Image
ከዚህ ቀደም በተለያየ ጊዜ በተዘጋጁ ሁለት ፅሁፎች፣ የድህረ መለስን ኢህአዴግ የኃይል አሰላለፍ ለማመልከት መሞከሬ የሚታወስ ቢሆንም፤ ዛሬም ያልተጠበቁ ክስተቶችን ማስተዋላችን አልቀረም፡፡ በርግጥ «አዲሱ የኢህአዴግ አሰላለፍ ፪» በሚል ርዕስ ቀርቦ በነበረው ተጠየቅ ከሞላ ጎደል ሀገሪቷን እንደንጉስ ሚካኤል ከጀርባ ሆነው የሚያሽከረክሯት ህወሓት እና ብአዴን መሆናቸው የተጠቀሰበት አውድ ብዙም አልተቀየረም፡፡ ይሁንና በኦህዴድ እና ደኢህዴን ውስጥ እየታየ ያለው የእርስ በእርስ መተጋገል መደምደሚያ ምናልባት ወቅታዊውን መልከአ ኢህአዴግ ሊለውጠው የሚችልበት አጋጣሚ እንዳለ እገምታለሁ፤ ማን ያውቃል? …እነዚህን ኩነቶች ታሳቢ አድርገን የገዢው ፓርቲ አክራሞትን በአዲስ መስመር ጨርፎ ወደመመልከቱ እንለፍ፡፡
የደቡብ ኢትዮጵያ «ብላቴኖች»
ክልሉን የሚያስተዳድረው የደኢህዴን የአመራር አባላት በስርዓቱ ልሂቃን የፖለቲካ ግምገማ ገና «ብላቴና» ተደርገው የሚወሰዱበት የትምክህት ዘመን አላከተመም፡፡ በርግጥ ድርጅቱ ደርግን ለመጣል በተደረገው የትጥቅ ትግል ላይ የተሳተፈ ባለመሆኑ፣ ዛሬም ፖለቲካን (ሀገር ማስተዳደርን) በበረሃው ትግል ተፈትኖ ከማለፍ ጋር ከሚያጋምዱት የግንባሩ ጉምቱ መሪዎች ዘንድ፣ ይህን መሰል ማጣጣያ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ለደኢህዴን ደካማነት በምክንያትነት የሚነሳው ጉዳይ ከአወቃቀሩ ጋር የሚያያዝ ነው፤ ይኸውም በክልሉ የሚገኙ 56 የተለያዩ ዘውጎችን ማቀፉ ለመከፋፈል አደጋ በቀላሉ የሚጋለጥበትን ዕድል የማስፋቱ እውነታ ነው፡፡ ይህም ሆኖ ከክልሉ ነዋሪዎች በቁጥር የሚልቁት የወላይታና የሲዳማ ተወላጆች፣ በደኢህዴን ውስጥ ያላቸው ተሰሚነት (ተፅዕኖ) የገዘፈ መሆኑን ለመረዳት፣ ሕገ-መንግስቱ ከፀደቀበት ጊዜ ጀምሮ የፓርቲውን ሊቀ-መንበርነትም ሆነ የክልሉ ፕሬዚዳንትነት ከሁለቱ ብሔሮች በቀር፣ ለሌሎቹ የሰማይ ያህል የራቀ ያደረገውን «ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት» መጥቀሱ በቂ ነው፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የፓርቲው ሊቀ-መንበር ኃይለማርያም ደሳለኝ የያዘውን መንግስታዊ ስልጣን የሚመጥን ተሰሚነት ለማግኘት ድርጅታዊ ድጋፍ ማሰባሰብ ላይ ያተኮሩ የሚመስሉ ክስተቶችን ሲከውን ታዘብናል፡፡ ኩነቱን በስነ-አመክንዮ ለማጠናከር ጥቂት ማሳያዎችን ላቅርብ፡- በጠቅላይ ሚኒስትርነት መንበር ላይ ከተቀመጠ በኋላ፣ በደኢህዴን ውስጥ ያሉ የተወሰኑ ተገዳዳሪዎቹን ከኃላፊነታቸው ከማንሳትም አልፎ፣ ደጋፊዎቹ (ታማኞቹ) እንደሆኑ የሚነገርላቸውን በከፍተኛ ሥልጣን ላይ አስቀምጧል የሚያስብለው፣ ከወራት በፊት በፓርቲውም ሆነ በደቡብ ክልል ከእርሱም የበለጠ ተሰሚነት የነበረውን ሽፈራው ሽጉጤን አንስቶ፤ ትጉህ አገልጋዩ እንደሆነ የሚነገርለትን ደሴ ዳልጌን ተክቶታል፤ በቅርቡ ደግሞ ሌላኛው ‹የደኢህዴን ቁልፍ ሰው› የሚባለው የፖለቲካ (የድርጅት) ጉዳይ ኃላፊ እና የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አለማየሁ አሰፋን ያለአንዳች ኮሽታ «በትምህርት ስም» ከቦታው አንስቶታል (ይህ ጉዳይ እስከአሁን ድረስ መንግስታዊው ሚዲያ የዜና ሽፋን አላገኘም)፡፡ በግልባጩ ታማኝነታቸውን ያስመሰከሩ፣ ከሲዳማ ብሔር ውጪ ያሉ ጓዶቹን በፌደራል መንግስቱ ወሳኝ የስልጣን እርከኖች ላይ አስቀምጧል፡፡ ለማሳያ ያህልም አሰፋ አብዩ /ሀድያ/፣ ወርቅነህ ገበየውን ተክቶ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር፤ ደበበ አበራ /ከፋ/፣ የኢህአዴግ ዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ፤ ውዱ ሀቶ /ሸካ/፣ የፀረ ሙስና ምክትል ኮሚሽነር፤ አማኒኤል አብርሃም /ወላይታ/፣ በሚኒስቴር ዴኤታ ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ አደረጃጀት አማካሪ፤ ሰለሞን ተስፋዬ /ጉራጌ/፣ በተመሳሳይ ማዕረግ የፕሬስ አማካሪ፤ ካይዛ ኬ (ጂንካ) በገቢዎች ባለስልጣን የገብረሀዋድን ቦታ ተክቶ የገባ እና የፌደራል ዋና ኦዲት መስሪያ ቤት ምክትል ኃላፊ ተደርጋ የተሾመችውን የወላይታዋ ተወላጅን መጥቀስ ይቻላል (ከደኢህዴን የሥራ-አስፈፃሚ አባላት መካከል የኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትሩ ሬድዋን ሁሴን እና መከላከያ ሚኒስትሩ ሲራጅ ፈጌሳም የሲዳማ ተወላጅ አለመሆናቸውን ልብ ይሏል) ይህንን ጉዳይ እንዲህ በብሔር ደረጃ ቁልቁል አውርደን እንድንመለከተው የሚያስገድደን ስርዓቱ ከሚያራምደው የፖለቲካ ፍልስፍና እና በክልሉ እየተነሱ ካሉ የማንነት ጥያቄዎች ጋር የመቆራኘቱ አንድምታ ነው፡፡ በተለይ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሲዳማዎች ራሳቸውን ችለው
በክልል ደረጃ ለመዋቀር ተደጋጋሚ ጥያቄ አቅርበው አያሌ መስዋዕትነትን መክፈላቸው ይታወሳል (በኢህአዴጋዊ የክልል አሰያየም ቀመር ሕገ-መንግስታዊ ድጋፍ ያላቸው መሆኑ ሳይዘነጋ)፡፡ ይሁንና ጥያቄው ተቀባይነት ቢያገኝ የክልሉ አስተዳደር መቀመጫ የሆነችውን አዋሳን ከመውሰዳቸውም በላይ፣ ሊያስከትል የሚችለው አለመረጋጋት ሲታከልበት፣ ህዳጣን ልሂቃኑን የኢኮኖሚ ጥቅመኝነት ያሳጣቸዋል፡፡ ይህ ስጋትም በደኢህዴን ውስጥ ከሲዳማ ተወላጆች ውጪ ካሉ የአመራር አባላት ድርጅታዊ ድጋፍ ለማግኘት ብርቱ ትግል ከሚያደርገው ኃይለማሪያም ደሳለኝ ጋር በወሳኝ ሰዓት፣ መሀል መንገድ ላይ ቢያስተቃቅፋቸው የማይታመን አይሆንም፡፡

የእነዚህ አዳዲስ ኩነቶች (ሹም ሽሮች) መግፍኤ፣ በሁለት የቢሆን ሃሳቦች ተነጣጥለው ሊታዩ ይችላሉ፡፡ የመጀመሪያው ኃይለማሪያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚንስትርነት ሹመቱን ተከትሎ ‹በዚህ ላይ ፈርም›፣ ‹ይህንን ተናገር›፣ ‹እንዲህ አይነት አስተያየት ስጥ!!› ወዘተ የሚሉ ከጀርባ ሆነው የሚሾፍሩት የአለቆቹ ቀጭን ትዕዛዛትን የሚገዳደርበት ፖለቲካዊ ጉልበት ለማሰባሰብ እና በቁርጥራጭ ጨርቅ በተጣጣፈው እናት ድርጅቱ ውስጥ ያሉ ችግሮችን ስልታዊ በሆነ መልኩ አስወግዶ ቅቡልነቱን ለማጠናከር እንቅስቃሴ ጀምሯል የሚል ሊሆን ይችላል፡፡
ሌላኛው ደግሞ ከኢትዮጵያውያንም አልፎ በውጪ ዜጎች ሳይቀር ‹ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሻንጉሊት ነው› የሚለውን እምነት ለማስቀየር በህወሓትና ብአዴን እየተደረገ ያለ ፖለቲካዊ ጨዋታ ሊሆን የመቻሉ ጉዳይ ነው፡፡
ኦህዴድ
ባለፉት የህወሓትም ሆነ የአቶ መለስ ዜናዊ የበላይነት በገነኑባቸው ዘመናት፣ ኦህዴድ ምንም እንኳን ስርዓቱን ካነበሩ የግንባሩ አባል ድርጅቶች አንዱ መሆኑ ባይካድም፣ በስጋት መታየቱ የአደባባይ እውነታ ነው፡፡ እንዲያውም በአንድ ወቅት አቶ መለስ ራሱ «ኦህዴድ ሲፋቅ ኦነግ ነው» ማለቱ አይዘነጋም፡፡ ከሶስት ያላነሱ የስራ አስፈጻሚ አባላቱ፣ ድርጅቱን ከድተው ኦነግን መቀላቀላቸውም የውንጀላው ማሳያ ተደርጎ እስከመወሰድ ደርሶ ነበር፡፡ ይህ ሁኔታም ኦህዴድን የተረጋጋ አመራር እንዳይኖረው ከማደናቀፉም ባሻገር፣ በተቀነባበረ ማኪያቬሊያዊ ሴራ እርስ በርስ በማይተማመኑና በተከፋፈሉ ሰዎች ስር እንዲቆይ አስገድዶታል፡፡ ግና፣ ኩነቱን ምፀት የሚያደርገው ህወሓት በረሃ እያለ ያሳትመው በነበረው ልሳኑ «የኦሮሞ ጥያቄና የኢትዮጵያ አብዮት» በሚል ርዕስ ባሰራጨው ፅሁፍ ኢህአፓን «የኦሮሞ ሕዝብ በነፍጠኛው ላይ የነበረውን ተገቢ ጥላቻ በማራገብ ፋንታ ለማብረድ በተጨባጭ ተንቀሳቅሷል» («የትግል ጥሪ» 3ኛ ዓመት ቁጥር 10፣ 1979 ዓ.ም) ሲል ይከስሰው እንደነበረ ማስተዋላችን ነው፡፡
በአናቱም አቶ መለስ እስከ ህልፈቱ ድረስ በኦህዴድ ደስተኛ እንዳልነበረ ይነገራል፡፡ ይህ ግን ‹የኦሮሞን ሕዝብ በአግባቡ አላገለገለም› ከሚል ቁርቆራ የተነሳ አይደለም፤ እንዲህ አይነቱ ስሜት ሌላውን ክልል ቀርቶ ትግራይንም የሚመለከት ቢሆን አሳስቦት አያውቅምና፡፡ የእርሱ ቅሬታ ‹ህዝቡን አሳምነውም ሆነ ጠርንፈው ከድርጅቱ ጎን አላሰለፉትም›፣ ‹ሁላችንንም በሚያሳጣ መልኩ ዘረፋ ውስጥ ገብተዋል›፣ ‹ዲሲፕሊን የላቸውም…› የሚሉና ሌሎች መሰል መነሾዎች ናቸው፡፡ እንዲህ ያለ የድርጅቱ «እንዝህላልነት» ደግሞ የህዝቡ ልብ ይበልጥ ኦነግን እንዲናፍቅ ማስገደዱን መለስ ዜናዊ ጠንቅቆ ያውቅ ነበር፡፡ ለዚህም ይመስለኛል የክልሉን ባለስልጣናት ሁሉ ወደ ጎን ብሎ እታች ድረስ በመውረድ የወረዳ አመራሮችን ቀጥታ ያለ ሥልጣን ተዋረድ በስልክ እስከማናገር የተገደደባቸው ቀናት የበዙት፡፡ በርግጥ በድርጅቱ ስብሰባዎች ላይ መተላለፍ ያለባቸውን ውሳኔዎች በፅሁፍ መስጠት እና ለአመራርነት የሚመረጡ ሰዎችን መመደብ ድረስ ባሉ ጉዳዮች ጣልቃ የመግባቱ ነገር ማንም አሌ የማይለው በግልፅ ይታይ የነበረ ክስተት ነው፡፡
የሆነው ሆኖ ከምንጮቼ እንዳረጋገጥኩት አባዱላ ገመዳ ዕድሜውን ሙሉ ሲፈራ የኖረው መለስ ዜናዊን ብቻ ነበር፤ መለስ ደግሞ ይህችን ምድር ለመጨረሻ ጊዜ ከተሰናበታት አንስቶ የተቆጠሩት በርካታ ወራት ፍርሃቱን ጥሎ ነፃነቱን እንዲጎናፀፍ ለመርዳት ያስችሉታል ብዬ አስባለሁ፡፡ እናም በዚህ መልኩ ተፈጥሮ ያመቻቸለትን ታሪካዊ አጋጣሚ ተጠቅሞ ይደቆስ የነበረውን ኦህዴድ ከወደቀበት ለማንሳት ሙከራዎችን እያደረገ ይመስለኛል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኦህዴድ በሚያደርጋቸው ስብሰባዎች ላይ የሚቀርቡ አንዳንድ አጀንዳዎችና አቋሞችን የአባዱላ ግፊት እንዳለባቸው ስናስተውል፣ «ጄነራሉ» ወሳኝ ሰው ለመሆን እያደረገ ያለው የጥንጣን ጉዞ ምን ያህል እየሰመረለት እንደሆነ ለመረዳት ያስችላል፡፡ ይህንን መከራከሪያ ከለጠጥነው ደግሞ፣ ከህወሓት/ብአዴን ጋር ትከሻ መገፋፋት ጀምሯል ወደሚል ጠርዝ ይገፋናል፡፡ ይህም ባይሆን እንኳ ከኃይለማርያም ደሳለኝ የተሻለ ተሰሚነት እንዳለው ለመናገር የሚያስደፍሩ ማስረገጫዎች አሉ፡፡ ጠቅላይ ሚንስትሩ ቀን የከዳ ዕለት በተናጠል በኃላፊነት ሊያስጠይቁት የሚችሉ ጉዳዮችን ሳይቀር፣ በያዘው ሕገ-መንግስታዊ ሥልጣን ከመወሰን ይልቅ በቡድን እንዲያልቅ ሲስማማ፤ በግልባጩ አፈ-ጉባኤው ከዚህ ቀደም በምክር ቤቱ ውስጥ ተነስተው ለአቶ መለስ ይቀርቡ የነበሩ ጉዳዮችን ወዲያውኑ መፍትሔ እንዲያገኙ በማድረግ ሲቋጫቸው ተደጋግሞ ተስተውሏል፡፡ ኦህዴድንም በሚመለከት ‹በድርጅታዊ መደጋገፍ› ስም ማንም ጣልቃ መግባት እንደማይችል በይፋ እስከ መናገር መድረሱን ምንጮች ጠቅሰውልኛል፡፡ በቀጣይ አመት የሚደረገውን አምስተኛ ዙር አገር አቀፍ ምርጫን አስመልክቶም እየተደረገ ባለው ዝግጅት በሃሳብ አመንጭነት እየተሳተፈ ነው፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት ለምክር ቤቱ የቋሚ ኮሚቴ አባላት፣ ከሁሉም የመንግስት መስሪያ ቤት ለተወከሉ እና ምርጫ ቦርድ ሀላፊዎች /ፕሮፌሰር መርጋ በቃና እና ዶ/ር አዲሱ ገ/እግዚአብሔር በተገኙበት/ «የአውራ ፓርቲ ዴሞክራሲያዊ ባህሪያት» በሚል ርዕስ ጥናታዊ ፅሁፍ ማቅረቡ አስረጅ ሆኖ ሊወሰድ ይችላል (በነገራችን ላይ ስርዓቱ በምርጫ ስም የሚፈፅመውን ደባ ፍንትው አድርጎ የሚያሳየው፣ ሁለቱ የቦርዱ ኃላፊዎች የዚህ አይነቱ ውይይት ላይ ተሳታፊ መሆናቸው ነው)፡፡ እንዲሁም ይህንኑ ጉዳይ በተመለከተ በአዳማ ለክልል አፈ-ጉባኤዎች ሰፊ ትንተና ሰጥቷል፡፡
የአባዱላ ገመዳንና የበረከት ስምኦንን መገፋፋት በጨረፍታም ቢሆን ሊያሳይ የሚችለው ሌላኛው ሁነት ደግሞ ወ/ሮ አና ጎሜዝን አስመልክቶ ሊነሳ የሚችለው ነው፡፡ በረከት «የሁለት ምርጫዎች ወግ» በሚለው መጽሐፉ «የቅኝ-ገዥነት መንፈስ ያልለቀቃት» ብሎ የገለፃትን አና ጎሜዝ (የመለስ በስድብ የተሞላ የኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጣ መጣጥፍ ሳይዘነጋ)፣ ከሁለት ወራት በፊት አዲስ አበባ

በመጣችበት ወቅት አባዱላ በጓዳዊ ስሜት እንዳስተናገዳት ራሷ ከመመስከሯም በዘለለ፣ እነርሱም በአዲስ ዘመን ጋዜጣቸው «እየተመካከርን ነው» የሚል የወዳጅነት መንፈስ የረበበበት የፎቶ ዘገባ ማቅረባቸውን እናስታውሳለን፡፡ ይህች ተራ የምትመስል ሁነት ለበረከት የምታስተላልፈው መልዕክት ቢኖር ‹እናንተ እንደሰይጣን የረገማችሁትን ሁሉ እየተከተልን አንረግምም» የምትል እኩዮች ነን አይነት ትከሻ መጋፋት ትመስለኛለች፡፡
በአናቱም አባዱላ አብዛኛው የኦህዴድ አመራርን በዙሪያው ማሰባሰብ ስለመቻሉ ይነገራል፡፡ ከዚህ ቀደም በአደባባይ እስከመዘላለፍ የተደራረሱትን አቶ ሙክታር ከድርንም ከጎኑ ማሰለፍ ችሏል፡፡ በአንድ ወቅት የግል ጠባቂው የነበረውና አሁን የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የሆነው አብይ አህመድ በእንዲህ አይነቱ ጊዜ ውለታ ለመመለስ የሚያደርገው ተጋድሎ የማይናቅ ጠቀሜታ አስገኝቶለታል፡፡ የሰሞኑ ሹም ሽርም የራሱ የሆነ አንድምታ አለው፡፡ ህጋዊ ባልሆነ መንገድ በማዕከላዊ ኮሚቴ ድምጽ ከስልጣኑ የተሻረው የክልሉ ፕሬዚዳንት አለማየሁ አቱምሳ (እርሱን ማንሳት የሚችለው ጠቅላላ ጉባኤው ብቻ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ በርግጥ ሰውየው አሁን አልፏልና በባህላዊ ልማዳችን መሰረት ነፍስ ይማር ብለን እናልፋለን) በ2002ቱ ምርጫ ማግስት አቶ መለስ ከካድሬዎቹ ይሁንታ ውጪ አባዱላን ለመተካት ያመጣው እንደነበር ይታወሳል፡፡ (በነገራችን ላይ በወራት እድሜ ውስጥ በመለስ የተሾሙ የክልል ፕሬዚዳንቶች ከኃላፊነታቸው ሲነሱ ከሽፈራው ሽጉጤ እና አያሌው ጎበዜ ቀጥሎ አለማየሁ አቱምሳ ሶስተኛው ሰው መሆኑ ነው) የድርጅቱ ሊቀ-መንበር እና ምክትል ሆነው የተመረጡት ሙክታር ከድርና አስቴር ማሞም የአባዱላን የበላይነት ለመቀበል ግለ- ሂሳቸውን ውጠዋል፡፡ ይህም ሆኖ የክልሉ አስተዳዳሪ ማን ይሆናል? የሚለው ጥያቄ ገና መልስ አላገኘም፡፡ ምናልባት (ከስራ አስፈፃሚዎችም መካከል መምረጥ እንደሚቻል ታሳቢ ተደርጎ) በሌሎች አካባቢዎች እንደታየው ከድርጅቱ ሊቀ-መናብርት (ሙክታርና አስቴር) አንዳቸውን መሾም ቢፈልጉ እንኳ ዕውን የሚሆንበት ዕድል የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱ የህዝብ ተወካዮች እንጂ የጨፌ ኦሮሚያ ም/ቤት አባል አይደሉምና፡፡ በእኔ ግምት እስከሚቀጥለው የምርጫ ዘመን ድረስ ቦታው አዲስ ሰው ሳይሰየምበት በምክትል ፕሬዚዳንቱ አብዱል አዚዝ ስር እንዳለ የሚቆይ ይመስለኛል፡፡
ከምርጫው በኋላስ? ….አፈ-ጉባኤው በኦህዴድ ውስጥ ለማስፈን እየሞከረ ካለው «አምልኮ አባዱላ» ተነስተን «ተገፈተርኩበት!» የሚለውን ያደረ ቁጭቱን ስንደምርበት ወንበሩን ራሱ ይይዘው ይሆናል ከሚል ጠርዝ ያደርሰናል፤ አሊያም ከሽርኮቹ ሙክታር ከድር እና ወርቅነህ ገበየው አንዳቸውን አሾሞበት በጨፌ ኦሮሚያም የሚካኤል ስሁልን መንፈስ ማንበሩ አይቀርም ብሎ ቅድመ ግምት ማስቀመጥ ይቻላል (ይህ መላምት የህወሓት-ብአዴን ጥንካሬ በዚሁ ከቀጠለ እና የእነርሱ ፍላጎት ደግሞ የተለየ ከሆነ ከህልም ሊዘል አለመቻሉን በማመን ላይ የተመሰረተ ነው)
ኦህዴድን ካነሳን የሌንጮ ለታን ኦዴግን መፃኢ እድልም መመልከት ግድ ይለናል፤ ምክንያቱም ኦዴግ አገር ውስጥ ገብቶ በሰላማዊ መንገድ መታገል ወስኖ ጨርሷልና፤ ሂደቱንም ለማመቻቸት ከግንባሩ መሪዎች አቦ ሌንጮ ለታ፣ ዶ/ር ሌንጮ ባቲ፣ ዶ/ር ዲማ ነጎዎ፣ ዶ/ር ታደሰ ኤባ እና ዶ/ር በየነ አሰቦ ጋር ከስምምነት ለመድረስ፣ ኢህአዴግ በውጪ ሀገር ከሚገኙት የጄኔራል ታደሰ ብሩ ልጆች በተጨማሪ፣ ፕ/ር እንድሪያስ እሸቴ፣ ፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅ፣ ፓስተር ዳንኤል፣ ሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ፣ ሻለቃ ደራርቱ ቱሉ፣ አባቢያ አባጆቢር፣ አቶ በቀለ ነዲ (የአዋሽ ባንክ የቦርድ ሰብሳቢ የነበሩ)፣ ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞንን የመሳሰሉ አደራዳሪዎችን ማሳተፉ ይነገራል፡፡
ይህም ሆኖ ድርድሩ በስኬት ተቋጭቶ ኦዴግ ሀገር ቤት መግባት ቢችል እንኳ፣ ኦህዴዶች ‹አያሰጋንም› የሚል እምነት እንዳላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ግና፣ ያለፉት ሁለት አስርታት ዘግናኝ ክስተቶች አሻራ ዛሬም በረዣዥሞቹ የባሌ ተራሮች በጉልህ ተቸክችኮ የመታየቱ እውነታ፣ በስርዓቱ ላኮረፈው የኦሮሚያ ህዝብ፣ ኦዴግን አማራጭ የሚያደርግበት «አኪር» ሸሽጎ ይዞ እንደሆነ ማን ያውቃል? ይህ እንግዲህ እነ ሌንጮ «ካዳሚ» ለመሆን አይመጡም በሚል ስሌት ከተቃኘ ነው፡፡ ይሁንና ከድርድሩ ጀርባ ያለውን እንቆቅልሽ ለመፍታት
ጊዜ የሚጠይቅ ቢሆንም፣ ጉዳዩን ውስብስብ የሚያደርጉ ክስተቶችን ግን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይኸውም በአፈ-ጉባኤ አባዱላ ፊት አውራሪነት ስር ለመጠናከር እየሞከረ ያለው ኦህዴድ፣ ከሰዎቹ ሀገር ቤት መግባት ምን ያተርፋል? ምንስ ያጣል? ከሚለው ጋር ይያያዛል፡፡
መቼም የኦዴግን መምጣት፣ ኦቦ ሌንጮ «እንጮቴ» (ተወዳጅ ባሕላዊ ምግብ ነው) በአይኑ ላይ እየተመላለሰ እንደሆነ ከሰነዘረው ቀልድም ሆነ «ከሌሎች የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ዘመናዊ ፌደራሊዝምን እመሰርታለሁ» ብሎ በደምሳሳው ከገለፀው ዓላማው ጋር አያይዞ ማለፍ አይቻልም፡፡ አሊያም ያኔ እርሱ ሸገርን ተሰናብቶ ሲወጣ ገና ያልፀደቀውን አንቀፅ 39ን «አስፈፅማለሁ» በሚል ቀቢፀ-ተስፋ ተገፍቶ ነው ማለትም አይቻልም፡፡ በግልባጩ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ‹የኦዴግ መሪዎች በኦነግ ዘመን ለእስር የዳረጓቸውን በሺ የሚቆጠሩ የኦሮሚያ ተወላጆችን ለማስፈታት ሲሉ፣ በታማኝ ተቃዋሚነት ለመታገል ወስነው ነው የሚመጡት› የሚለውን መከራከሪያቸውን ለመቀበል የሚቸግረው ደግሞ፣ እስረኞቹን መፍታት ለሃያ አመታት ያህል በክልሉ ላይ ሰላማዊ ዜጎችን በማሰር የሚታወቀውን ኦህዴድን ሊያሳጣ የመቻሉ ነገር ነው፡፡ ያም ተባለ ያ፣ «ለሁሉም ጊዜ አለው» እንዲል ጠቢቡ

ሰለሞን ሁሉም ቋጠሮ ጊዜ የሚፈታው ይሆናል፡፡ አሁን ላይ እርግጠኛ መሆን የሚቻለው በኦህዴድ ውስጥ አባዱላ ገመዳ ወሳኝ እየሆነ የመምጣቱ እውነታ ብቻ ነው፡፡
ህወሓት-ብአዴን
በዋናነት ሀገሪቷን እንደሚያሽከረክሯት የሚነገርላቸው ህወሓት እና ብአዴን፣ በመጪዎቹ ጊዜያት ‹ኢህአዴግ ለዳግም ክፍፍል ሊዳረግ ይችላል› በሚል ፍርሃት ድርና ማግ ሆነው እየሰሩ ስለመሆኑ እየሰማን ነው፡፡ በርግጥ ‹መለስ ህወሓትን አዳክሞ ነው ያለፈው› የሚል የትግርኛ ተናጋሪዎች ድምፅ መሰማት ከጀመረ ሰነባብቷል (በነገራችን ላይ ከ2000 ዓ.ም ወዲህ የህወሓትን የምስረታ በዓል የካቲት 11ን በብሔራዊ ደረጃ ማክበር መቅረቱን በይፋ ከማወጃቸውም በላይ፣ መለስ ራሱ ለመጨረሻ ጊዜ በመቀሌው የሰማዕታት አዳራሽ የተገኘው 35ኛው ዓመት በተከበረበት ወቅት ነበር፡፡ ይሁንና ከህልፈቱ በኋላ ድርጅቱ የደረሰበትን ድክመት ለመሸፋፈን በደመቀ መልኩ እያከበረው ይገኛል፤ ለዚህም ይመስለኛል በአምናውም ሆነ በዘንድሮው በዓል ላይ ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ መቀሌ የሞቀ ተገኝቶ ንግግር ከማድረግም አልፎ ከሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኡመር ሀሰን አልበሽር ጋር በትግሉ ዘመን በተቀነቀኑ ዜማዎች ሲደንስ በቴሌቪዥን መስኮት ተመልክተን ሦስተኛው ሚሊንየም ገባ እንዴ? ብለን ግራ የተጋባነው፡፡ አልበሽርስ አንድ ቻርተር አውሮፕላን ለክልሉ በስጦታ ያበረከተው ዕውን በዓሉን አስመልክቶ ነው? ወይስ በምትኩ የተሰጠው ነገር ኖሮ? መቼም የህወሓት የምስረታ በዓል እንዲህ ሊያስፈነጥዘው እይችልም)
‹ህወሓት ተዳክሟል› የሚለውን ቅሬታ የሚያሰሙ የቅርብ ሰዎች፣ ድርጅቱ አቅምና ልምድ በሌላቸው መሪዎች ስር ማደሩን ይጠቅሳሉ፡፡ ተስፋ የጣሉበት ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤልም ቢሆን ከአምባገነንነቱም በላይ ሀሳቡን አፍታቶ የማስረዳት ችሎታው ደካማ መሆን መፍትሄውን አርቆ ሰቅሎታል፡፡ እንደ ድርጅቱ የቅርብ ሰዎች አገላለፅ የ«ጠንካራ ተተኪ» አልቦነትን ለመረዳት፣ በቅርቡ ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ኃላፊነቱ በተነሳው አቶ ዘርዓይ አስገዶም ቦታ ላይ የዋልታ ስራ አስኪያጅ መመደቡ እና ራሱ ዘርዓይም በጓሮ በር የብሮድካስት ባለስልጣን ሆኖ መሾሙን (አዲስ ፊት አለመታየቱን) መመልከቱ በቂ ነው፡፡ በቅርቡ የዶክትሬት ዲግሪውን ያገኘው አርከበ እቁባይም ለአመራርነት ለቀረበለት ጥያቄ እያንገራገረ እንደሆነ ተሰምቷል፤ አቦይ ስብሃት ነጋም ኢ-መደበኛ በሆነ የጠረጴዛ ወግ ህወሓት «በግብር በላ» መሪዎች እጅ መውደቁን በቁጭት መናገራቸው ይጠቀሳል፡፡ ይሁንና በዚህ ቀውጢ ወቅት ሁለት ተቋማት ድርጅቱን ለጊዜውም ቢሆን ፖለቲካዊ ጉልበቱን እንዳይነጠቅ ታድገውታል፡፡ ደህንነቱ እና ሰራዊቱ፡፡
የሆነው ሆኖ ህወሓት ዛሬም ከብአዴን ጋር በማበር (በአባይ ፀሐዬ እና በበረከት ስምኦን የፊት መሪነት) የፖለቲካው አሽከርካሪነቱን እንዳስከበረ ይገኛል፡፡ ሁለቱ ሰዎች የስርዓቱን ርዕዮተ-ዓለምንም (በተለይም አብዮታዊ ዲሞክራሲን) ከሌሎች ጓዶቻቸው በበለጠ ማብራራት እንደሚችሉ ይነገራል፡፡ በጅጅጋ ከተማ የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በተከበረበት ወቅትም ሆነ ከሳምንታት በፊት በመቀሌ ከተማ በተዘጋጀ መድረክ አባይ ፀሐዬ የርዕዮተ-አለሙ «ተንታኝ» ሆኖ የቀረበው ከዚህ አኳያ ነበር፡፡ በአናቱም አባይ እና በረከትን ጨምሮ ከኦህዴድ ኩማ ደመቅሳ፤ ከደኢህዴን ዶ/ር ካሱ ኢላላ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፖሊሲ ጥናትና ምርምር አማካሪ ሆነው መሾማቸው ይታወሳል፡፡ በዋናነት ለኢህአዴግ የስልጣኑ መሰረት (ከታጠቀው ኃይል እና ኢኮኖሚያዊ ጥንካሬው በተጨማሪ) ‹በልማታዊ መንግስት፣ በጥርነፋ፣ ሳር-ቅጠሉን በማደራጀት፣ የብሔር ጉዳይን በማጎን እና መሰል ጭብጦችን በማስጮኽ የሚያምታታበት ርዕዮተ-ዓለሙ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የእነ በረከት የተሰሚነት ምስጢርም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በርግጥም የካቲት 14 ቀን 2006 ዓ.ም. የተሰበሰበው የሚኒስትሮች ምክር ቤት የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ማዕከልን ለማቋቋም የሚያስችል ደንብ ማፅደቁን እና የአራቱም ድርጅት የአ&#4632

Image

ከዚህ ቀደም የብርሃኑ አባነጋን መንሸራተት አስመልክቶ የፖለቲካ ሽርሙጥና እንደሆነና ግለሰቡም የፖለቲካ ዝሙት በመፈጸም ላይ እንደሆነ ቢገለጽም ሰሚ ጆሮ ለማግኘት አልታደልንም :: አዎ እንደ ግንቦት ሰባት እና እንደኢሳት ያሉ የዲያስፖራው መስታዎቶች ሊያዳምጡን ፍቃደኛ ካለመሆናቸውም በላይ እነሱ የሚያዳምጡት የወያኔን ዝሙተኛ ፖለቲከኞችን ስለሆነ መለማመጥን አንፈልግም:; ደስ ካላቸው ደስ ይበላቸው ደስ ካላላቸው ገደል ይግቡ ….. እኛ ግን ኢትዮጵያዊነታችንን የሚነጥቀን በነጻነት የምንተነፍሰውን ሃሳብ የሚገድብ ምንም ነገር አይመጣም…. እኛም አናቆምም …

በመጀመርያ ደረጃ ማወቅ ያለብን ነገር ቢኖር በሻእቢያ እና በወያኔ መካከል ከፍተኛ የሆነ የመረጃ ልውውጥ በፓርቲ ደረጃ እንደሚካሔድ እና ሁለቱ ጸረ ኢትዮጵያ አቋማቸው ያንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ መሆኑ ልንቀበለው የሚገባ ጉዳይ ነው:: አለም ሰልጥኖ ወደ አንድነት በማምራት በሰው ልጆች መካከል ያለ የቀለም እና የዘር ልዩነትን ለማጥፋት እና በቴክኖሎጂ እውቀት ተመንጥቆ ለመሄድ በሚሰራበት ዘመን በኢትዮጵያ ውስጥ ባረጀ እና ባፈጀ የጎሳ ፖለቲካ ጥያቄ ህዝብም ውስብስብ መንገድ ላይ በመጠላለፍ ለመከፋፈል እና ጠንካራ ሃገራዊነትን ለማዳከም የሚሰሩ ስራዎችን ልብ ብለን ማጤን እንዳለብን ለማስታወስ እገደዳለሁ:;

ብርሃኑ ዳምጤ አሊያም አባመላ በመባል የሚታወቀው የፖለቲካ ግልሙተኛ እና ሴሰኛ ግለሰብ ማረፊያ ያጣበትን ተሌኮ ለማስፈጸም በሚያደርገው መራወጥ ውስጥ ራሱን ግንቦት ሰባት ብሎ ከሚጠራው ድርጅት ጋር የፖለቲካ ዝሙት ሲፈጽም ቆይቶ በሁለት ስለት ቢላዋ በማረድ የራሱን እና የሌሎችን ደም በአደባባይ ለማፍሰስ ቆርጦ የተነሳ እና ያልተሳካለት ግለሰብ ነው::
ማወቅ ያለብን ነገር ቢኖር ይህ ግለሰብ ትክክል ነው ይህ ግለሰብ ትክክል አይደለም የሚለው ነገር እንደተጠበቀ ሆኖ የደፈረሰው መጥራት እንዳለበት በግልጽ ለመናገር እፈልጋለሁ::

ብርሃኑ ዳምጤ አባመላ በሚለው የፓልቶክ ፕሮግራሙ አጀማመሩ የወያኔን በልማታዊነት ሽፋን የሚሴረውን የጎሳ ፖለቲካ እና የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ በዲያስፖራው ውስጥ ለማስረጽ የፕሮፓጋንዳ ስራ ሲሰራ ቢቆይም ሊሳካለት አለመቻሉ ጸረ ወያኔ አቋም እንደያዘ ተደርጎ በሰርጎ ገብነት ከወያኔ በወረደለት ትእዛዝ አባካኝነት እና ከሻእቢያ ጋር በተደረገ የመረጃ ልውውጥ በሻእቢያ የነገር አባትነት ከግንቦት ሰባት ንቅናቄ ጋር የፖለቲካ ዝሙት እንዲፈጽም ተደረገ:: የፖለቲካ ዝሙቱ በእርካታ ታጅቦ በኢሳት የሳምንቱ እንግዳ ሆኖ ወያኔ በማሳጣት እና በመዝለፍ በሰርጎ ገብ የቆረጣ ታክቲክ የኢሳት ጋዜጠኞችን በማወዳደስ ግንቦት ሰባትን በማንቆለጳጰስ ራሱን ከተቃዋሚዎች ጎራ አሰልፎ የነበር ሲሆን እንዲሆን አክራሪዎች አሸባሪዎች ሲላቸው የነበረውን የኢትዮጵያውያንን ሙስሊሞች ትግል ለመጠጋት በመሞከር ቢያሞጋግስም አናቱን በፍልጥ ስላልነው ሳይሳካለት ቀርቶ አፉን ይዞ ተቀመጠ:: ዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሲኖር ከነበረው ከጃዋር መሃመድ ጋር ማታ ማታ ሻይ ቡና እያለው የኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎችን ፖለቲካ በማጥላላት እና በወያኔ የጎሳ ፖለቲካ ሲያጠምቀው የነበረው አባመላ ዞር ብሎ አዛኝ በመምሰል በጃዋር መሃመድ ላይም ጸር የሆኑ ቃላቶችን ሲተፋ እንደነበር ሲታወቅ አባመላ ራሱ ጃዋርን በጥላቻ ሲያሰለጥነው እንደነበር የማይዘነጋ እውነት ነው::

ግንቦት ሰባት ንቅናቄ ብሎ ራሱን የሚጠራው ድርጅት ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያውያንን እንደማይወድ እና ከጀርባው በሻእቢያ እየተጠመዘዘ የጸረ ኢትዮጵያ አቋም ማራመጃ መሆኑ የማይካድ ሃቅ ነው:: እንደ ኢሳት ባሉ በዲያፖራው ሃብት በሚተዳደሩ ሚዲያዎች የፖለቲካ ትግል እና የለውጥ አማራጭ ሃሳብ ያላቸው ኢትዮጵያውይና እንዳይቀርቡ እና እንዳይጠቀሙ በማገድ የወያኔ ትርፍራፊ የፖለቲካ ጋለሞታዎች እንዲዘፍኑበት መደረጉ አሌ የማይባልበት ጉዳይ ሲሆን በዚህ ጉዳይ ላይን ራሱ የሚዲያ ነጻነቶችን በመጋፋት ለውጥ ከማምጣት ይልቅ ነጻነቶች በሻእቢያና ወያኔ ተላላኪዎች በተዘዋዋሪ ሲቀበሩ እያየን ነው::

እንደ ግንቦት ሰባት ያሉ ድርጅቶች በፖለቲካ አማራጭ ሃሳብ የያዙ እና ለውጥ በማምጣት ረገድ ሚና መጫወት የሚችሉ ኢትዮጵያውያንን በመግፋት የወያኔ ሰርጎ ገብ ወንበዴዎችን በአመራር እና በድርጅታቸው የደህንነት መዋቅር ውስጥ በማስገባት ራሳቸውን ከትግሉ ውጪ ለመጠለዝ እየተወራጩ ይገኛሉ:; ኢሳት የሚዲያ ተቋም ተብሎ እስከተቋቋመ ድረስ ማድረግ የሚገባውን የማያውቅ እና ባልበሰሩ ሰዎች እና የጋዜጠኝነት ልምድ ባሌላቸው እንዲሁም በሳል እና ሚዛናዊ መረጃዎችን ባልያዙ ደረቅ ተንታኞች ታጅቦ የሞት ጉዞውን እያፋጠነ ነው::

ወያኔ በብርሃኑ ዳምጤ በኩል በአባቱ ሻእቢያ አዝማችነት የመጀመሪያ ዙር ስራውን አጠናቆ ብርሃኑ ዳምጤን ወደ ልማታዊ ጋዜጠኝነት መልሶታል:; በሃገር ወዳድነት ሽፋን በማስመሰል የተካነው ብርሃኑ ዳምጤ ድራማውን አጠናቆ ዲያስፖራ ተቃዋሚዎችን በመዝለፍ ስራ ላይ ተመልሶ ተሰማርቷል:: ካሁን በኋላ የአባመላ ፓልቶክ እንግዶች እንደ ጃዋር እና ዘርኣይ ያሉ የጥላቻ ፖለቲካ ስልጥኡኖች ናቸው:;ከሃገር ቤት የተሰራውን የወያኔን ድራማ እና የሚሚ ስብሃቱን ጸረ ግንቦት ሰባት እና ኢሳት ውንጀላ እና ትችት ተከትሎ የብርሃኑ ዳምጤ ትፋት ምን እየተሰራ እናዳለ እና የዲያስፖራውን የለውጥ ፖለቲካ ገደል ለመክተት በህዝብ የመኖር ህልውና ላይ ፍርሃት እና ሽብር ነዝቶ ወያኔን በስልጣን ለማቆየት የተሸረበውን ሴራ በገሃድ ያሳያል::

ከዳዊት ከበደ እና ከጃዋር የሰርጎ ገብ ፖለቲካ ያልተማሩት ግንቦት ሰባት እና ኢሳት ሃገር ወዳድ እና ብዙ ስራዎችን ሊሰሩ የሚችሉ ኢትዮጵያውያንን ወደ ጎን በማግለል በዙሪያቸው እንደብርሃኑ ዳምጤ ያሉትን ሰርጎ ገቦች በመኮልኮል ያላዋቂ ሳሚ … ሆነው ህዝቡን … በመለቅለቅ ላይ ይገኛሉ::ኢሳት አንድ ሃገር ወዳድ የሆነ ኢትዮጵያዊ በፕሮግራሞቹ ላይ ከማቅረብ ይልቅ የወያኔ ኮልኮሌ የመረጃ ሰዎች እና ሰርጎ ገቦችን ቢያቀርብ ያተረፈ እየመሰለው በፖለቲካ ኪሳራ ውስጥ ገብቶ ከሕዝብ ልሳንነት ይልቅ የግንቦት ሰባት ልሳን እንደሆነ እያንጸባረቀ ነው:: ኢህኣፓ በተፋቻቸው እንደ ብርሃኑ ነጋ ባሉ የፖለቲካ ሰልባጆች ትእዛዝ የሚመራ አስመስሎበታል:: እንደ ነእመን ዘለቀ ባሉ በሻእቢያ እና ወያኔ ትራፊዎች የሚመራው ኢሳት አጀማመሩ መልካም ቢመስልም ግን በጀት አይለቀቅልህም ከወያኔ ከዳሁ የሚሉ ግለሰቦችን እያባዛህ ካላቀረብክ የተባለ ይመስል ነጋ ጠባ የምናያቸው የወያኔ ሰዎችን መሆኑ አሳሳቢ አድርጎታል::ስለዚህ ግንቦት ሰባት እና ኢሳት ከወያኔ ሰርጎ ገቦች ጋር የፖለቲካ ዝሙት እየፈጸሙ የህዝብን ትግል እየገደሉት ነው ቢባል ድፍረት አይሆንም:: ለዛሬ በዚህ ይብቃ ጹሁፉ ቀጣይ ነው ይጠብቁት::

የ ‘11% እድገታችን’ ከሚታየው ነባራዊ ሁኔታ ጋር ሲነጻጸር
Sebhat Amare( Norway)
March 9,2014

እንደሚታወቀው በአንድ ሃገር የኤኮኖሚ፣ የፖለቲካና የማህበራዊ ክንውኖች የቀን ተቀን ለውጥ ውስጥ የህብረተሰብ ተሳትፎ(አስተዋጽኦ) ጉልህ ሚና አለው፡፡ እንዲሁም በሂደቱ ውስጥ የሚያጋጥሙ አገራዊ ጠቀሜታ ያላቸው ጉዳዮችም ይሁኑ ወይም በተቃራኒው የሚከሰት ተፈጥሯዊም ሆነ በመልካም አስተዳድር ችግር ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮች ዞሮ ዞሮ ከህብረተሰብ ጫንቃ ላይ አይወርድም፡፡ ይህ ስለሚታወቅ ሃላፊነት የሚሰማቸው፣ ለሃገርና ለሕዝብ ታማኝ የሆኑ፣ በሕዝብ ይሁንታ ስልጣን የያዙ መንግስታት ያላቸው ሃገሮች በየትኛውም ሃገራዊ እንቅስቃሴ ላይ ሕዝባቸውን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተሳታፊ በማድረግ በብሔራዊ ስሜት የታነፀና በሃገሩ ጉዳይ ላይ ቅንጣት ታህል የማያመነታ ብርቱ ህብረተሰብን ይገነባሉ፡፡ የእንደኛ አይነቶቹ የሃገርና የሕዝብ ፍቅር የሌላቸው አምባገነን የወያኔ መሪዎች ግን እንኳን ‘የሃገርህ ጉዳይ ያገባሀል’ ብለው ሊያሳትፉት ቀርቶ የአንድን ሕዝብ የዴሞክራሲ መሰረት የሆነውን የመናገርና ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ ተፈጥሮዊ የሆነውን መብቱን እንኳ ገፍፈው ሃገሪቱን የቁም እስር ቤት አድርገዋታል፡፡

የወያኔ ጁንታ ‘11% እድገት አሳይተናል’ እያለ በሌለ ተስፋ ላይ ተቀምጦ በሚኮፈስበት እና ሳተላይት ልናመጥቅ ነው፤ አውሮፕላን ፈበረክን፤ ልማታዊ መንግስት ……. እያለ ትምክህቱን በሚያሳይበት በአሁን ወቅን በሃገራችን መኖር ያልቻልን ኢትዮጵያውያን ድንበር አቋርጠን በተፈጥሮ የበለጸገች ሀገራችንን ጥለን ወደ ተለያዩ ሀገራት በስደት ተበትነን እንገኛለን፡፡ በአንጻራዊ የተሻለ የመኖርያ ቦታ ፍለጋ ለስደት የወጣው ወገናችን ያሰበበት ቦታ ሳይደርስ በበረሃ አሸዋ የተበላውና በባህር ሰጥሞ የቀረውን ቤቱ ይቁጠረው፡፡ እንደ ሰው አንድ የያደርገን ባሕርይ፤ እንደ ኢትዮጵያዊነትም ሁላችንንም የሚመለከተንና የፖለቲካም ሆነ የሃይማኖት ልዩነት ያልታየበት በደል ባለፈው ሰሞን በሳዑዲ ዐረብያ ግዛት እንደተፈጸመን መጥቀስ በቂ ነው። የጥቃት ዒላማዎቹ ኢትዮጵያውያን ናቸው። የጥቃቱ ልክ የለሽነትና አሰቃቂነት ደግሞ ይበልጥ የጎላው በሴት እህቶቻችን ላይ ነው። የዱር አውሬ እንኳን ከዚህ የተሻለ ክብር አለው። እነዚህ እጅግ ኋላ ቀር የሆኑ አረመኔዎች ከእንስሳ እንኳን አንሰው አንዲት በፍርሃት ነብሷን የሳተችን ሴት የሚደፍሩትን እያየን የተደፈሩት ‘ህጋዊ’ ናቸው ‘ህገወጥ’ የሚል የሕግ አንቀጽ መረጣ ውስጥ ልንገባስ እንዴት ይቻለናል? ህዝባችን እረኛ እንደሌለው መንጋ ተበትኖ፤ ተዋርዶና ክብሩን ጥሎ መኖር ከጀመረ እነሆ 23 አመታትን አስቆጠሯል፡፡ ዜጎቻችን በቄያቸዉ በሰላም ሰርተዉ እንዳይኖሩ በወያኔ አረመኔያዊ አገዛዝ መሬታቸውን ተቀምተውና ተማርረው በስደት የበረሀና የባህር ሲሳይ እየሆኑ ከዛም የተረፉት ይኸዉ አሁን እንደምናየዉ በጨካኝ መንግስታት ፖሊሶች ለእንግልት እና ለአሰቃቂ ሞት ተዳርገዋል፡፡ በሰለጠነ ዘመን ወደኋላ እንደ ጋርዮሽ የጨለማ ዘመን በወገኖቻችን ላይ በአረብ ሀገራት መንግስታት የሚደርሰዉን እንግልት የአለም አይን እና ጆሮ እንዲያይ እና እንዲሰማዉ በየቦታው ባሉ የሳዑዲ ኤምባሲዎች የተደረጉት ሰላማዊ ሰልፎች በመጠኑም ቢሆን የአለም ህዝብ ችግሩን እንዲረዳ ለማድረግ አስችሏል፡፡

”ነፃነት፣ አንድነት፣ ፍትህ እና እኩልነት በወሬና በዲስኩር አይመጣም” እንደተባለው የመስዋዕቱ አይነት ይለያይ እንጂ አነሰም በዛም ለነፃነት የሚደረግ ትግል ወይ ሃብትን ወይም የህይወት መስዋዕትነትን ይፈልጋል፡፡ ይህንን ሁሉ በህዝብና በሃገር ላይ የሚደርሰውን ለከት ያጣ ጭቆና የምናይ እና የምንሰማ በተለይ በሰለጠነው አለም የምንኖር ወገኖች እኛ በሰው ሃገር የምናገኘውን እንዲህ ያለውን የመፃፍ፣ የመናገር፣ የመሰብሰብና ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት ወገናችን በገዛ ሃገሩ ሲያጣ፣ ይህ ነው የማይባል ችግር ሲወርድበት በተግባር መልካም ውጤት የሚያመጣ ስራ ለመስራት ቆርጠን ልንነሳ ይገባል፡፡ በአንድነትና በቁጭት ለሃገራችን ህዝብ ነጻነት ካልተነሳን በስተቀር የወያኔን ተንኮል ችላ ማለት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የወገኖቻችንንና የውዲቱ ሃገራችንን የመከራ ጊዜ ማራዘም ማለት ነው፡፡ ዘረኛው ወያኔ በነፃ አውጪ ስም ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ እንዲሁም ከዛም በፊት የሚከተለው የተሳሳተ የኢትዮጵያን ሉዐላዊነት የማፍረስና የመበተን የመገነጣጠሉንና ብሔራዊ ጥቅምን አሳልፎ ለባዕዳን የመስጠቱን እኩይ ተግባር መመልከት የተለመደና የቀን ከሌት ክንውናቸው መሆኑ በሃይል ስልጣን ከያዙበት ጊዜ ጀምሮ እስከዛሬዋ ዕለት የሚታይ እውነታ ነው፤ ለዚህም ለማስረጃ ያህል ሰሞኑን በስፋት እንደሚወራው የ’ድንበር ማካለል’ ስም ተሰጥቶት የምዕራቡን የሃገራችንን ክፍል ለሱዳን አሳልፈው መስጠታቸውን መጥቀስ ይቻላል፡፡ በኢትዮጵያችን መልካም አስተዳደር ጠፍቷል፤ ሙስና እንደ ሸረሪት ድር በየቦታው አድርቷል፤ ‘የሕግ የበላይነት አለ’ በሚባልበት አገር ፍትህ ርቋል፤ ዘረኝነትና ጎጠኝነት ከመቼውም በላይ ተንሰራፍቷል፤ በሕገ መንግሥት የተረጋገጡ መብቶች ተጨፍልቀዋል፡፡

በነፃነት በመኖር የምንቀድማቸው ሃገራት ሰልጥነው በዴሞክራሲያዊ ስርዓትና መልካም አሰተዳደር የህዝቦቻቸውን ሰብዓዊ መብት ለማስጠበቅ ደፋ ቀና በሚሉበት በዚህ ዘመን የኋሊት የሚጓዘው ከዘመኑ ጋር መዘመን ያቃተው ወያኔ ከብዙ ዘመናት በፊት በነበረው ኢትዮጵያዊነትን የማፍረስ አስተሳሰብና የሃይል አምባገነናዊ አገዛዝ ተሸብቦ ያላስነባው ህዝብ፤ ያልጣሰው ህግና ስርዓት፤ ያላፈረሰው አንድነት፤ ያላዋረደው የህዝብ ስብዕና፤ ያልገባበት የእምነት ተቋም፤ ያልበተነው የሞያ ማህበራት፤ ያልገደለው፣ ያላሰረውና ያላስለቀሰው የህብረተሰብ ክፍል የለም::

ባለፉት አመታት በወያኔ አገዛዝ በግልጽ እንዳየነዉ የኢትዮጵያ ህዝብ እኩልነቱን፤ መብቱንና ነጻነቱን ለማስከበር የሚያደርገውን ትግል ለማኮላሸት እርስ በርሱ የሚቃረኑ ህጎችና መመርያዎችን አርቅቆ አያጸደቀ ሠላማዊ ዜጎችን አስሯል፤ አንገላቷል፤ ገድሏል፤ ከአገር በግፍ እንዲሰደዱም አድርጓል። ይሄንኑ የወያኔን ግፍ የአሜሪካ መንግሥት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤት እ.ኤ.አ በ2013 ዓ.ም በኢትዮጵያ ተፈፀሙ ያላቸውን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሪፖርት ሰሞኑን አውጥቷል፡፡ በሪፖርቱ የተካተቱት የመብት ጥሰቶች በህዝባችን ላይ በተደጋጋሚ እና በከፍተኛ ሁኔታ ወያኔ እያደረሰ ያለውን ግፍ በእማኝነት ያሳየ ሪፖርት ነው፡፡ የአሜሪካ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በሪፖርቱ ያካተታቸው እንደተጠበቁ ሆኖ፤ በወያኔ የተፈጸሙ እና እየተፈጸሙ ያሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ከዚያም የላቁ እንደሆኑና ሃገራችንና ህዝቧ ምን ያህል ውጥንቅጥ ውስጥ እንዳለን ያሳየ ሪፖርት ነበር፡፡

ኢትዮጵያ ሃገራችን ሀሳብን በነፃነት ያለፍርሀት መግለፅ የማይቻልባት፤ የዜጎች የኑሮ ደረጃ ከዕለት ዕለት እየተባባስ የሚሄድባት፤ ዘመናዊ የመረጃ መገናኛዎች ሆን ተብለው የታገዱባት፤ የህዝቦቿን ጥንታዊና ብርቅዬ የሆነውን መከባበርና አንድነት በዘር ጥላቻና በሀይማኖት ለመከፋፈል አገዛዙ የሚጥርበት፤ ዜጎች አለአግባብ የሚታሰሩባት፣ የሚገደሉባት፤ ዜጎች በከፍተኛ ሁኔታ የሚሰደዱባት፤ ነፃ፣ ፍትሐዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ያልተካሄድባት፤ ዜጎች ከመኖሪያቸውና ከቀዬአቸው የሚፈናቀሉባት፤ ለሕግ ተገዢ ያልሆነ መንግሥት ያለባት፤ ዜጎች የገዢው ፓርቲ አባል ካልሆኑ በስተቀር በነፃነት ሠርተው መኖር የማይችሉባት፤ ነፃ ሚዲያ የሌለባት፤ ዜጎች ለሀብት ንብረታቸው ዋስትና የማያገኙባት፤ ህዝባዊ መንግሥት የሚናፍቅ ህዝብ ያለባት፤ በሀገሪቱ የሚገኙ ሁሉም ተቋማት የገዢው ፓርቲ ፖለቲካዊ መጠቀሚያ የሆኑባት፤ ቤቶች በቁመታቸው ማደጋቸው እንደዕድገት የሚቆጠርባት ሀገር ሆናለች። ስለሆነም ኢትዮጵያንና ህዝቧን ለመታደግ በየትኛውም የትግል መስክ ተሳትፎ በማድረግ ለነፃነት፣ ለፍትህ እና ለእኩልነት በሚደረገው ትግል ውስጥ የየራሳችንን አሻራ ለማሳረፍ ለተግባራዊ ትግል እንትጋ፡፡

ለዚህ ሁሉ በሃገርና በህዝብ ላይ ለሚደርሰው እንግልትና መዋከብ ምንም እንኳን የመንግስትን እርካብ የተቆናጠጡት ’ገዢዎቻችን’ ከተፈጥሮ ባህሪያቸውና የኢትዮጵያን ሉዐላዊነት ከማፍረስ አንፃር የፈለጉትንና ያሻቸውን ቢያደርጉም በየግዜው በህዝብና በሃገር ላይ የሚያደረሱትን ሰቆቃ የየሰሞኑ መነጋገሪያ ከማደረግ በዘለለ በአንድነት በማበር በደል በቃኝ፣ ግፍ በቃኝ፣ መሰደድ በቃኝ፣ መታሰርና መገረፍ በቃኝ፣ ከሃብትና ከቀዬ መፈናቀል በቃኝ ብለን ለለውጥ እንድንነሳ በህብረት በመስራት ውዲቱ ሃገራችንን ከውድቀትና ከጥፋት ለማዳን የኢትዮጵያዊነት ሃላፊነታችንንና ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

ኢትዮጵያ ሀገራችን ለዘለዓለም በክብር ትኑር !!

የፓትርያርኩ የለውጥ ተግዳሮትና ተስፋ – በአንደኛ ዓመት በዓለ ሢመት ዋዜማ

የብልሹ አሠራርና ሙስናን ችግር በዐደባባይ የተናገሩ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ናቸው
ፓትርያርኩ ጽኑ አቋም ስለሌላቸው ለጣልቃ ገብነት የተመቹ ኾነዋል
ጣልቃ ገብነቶችን መቋቋምና የቅ/ሲኖዶሱን የውሳኔ ልዕልና ማስከበር ይጠበቅባቸዋል
ፓትርያርኩ ዙሪያቸውን መፈተሽ አለባቸውብቃት ያለው የአማካሪ መዋቅር ያስፈልጋቸዋል

Image

የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ፤ ለስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ከቀረቡት አምስት ዕጩዎች መካከል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማትያስ በከፍተኛ ድምፅ መመረጣቸው ተነገረ። ሊቀ ጳጳሱ በቤተ ክርስቲያኒቱ የፓትርያርኮች ምርጫ ታሪክ ከፍተኛውን የመራጮች ድምፅ በማግኘት አሸናፊ መኾናቸው በተገለጸበት ወቅት የብዙዎችን ትኩረት በሳበ ኹኔታ በመስቀላቸው ሲያማትቡ ታዩ።
የወቅቱን ስሜታቸውን አስመልክቶ ‹‹ዜና ቤተ ክርስቲያን›› በተሰኘው መጽሔት ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ÷ ‹‹ፓትርያርክ እኾናለሁ የሚል መንፈስ በውስጤ ስላልነበረ ውጤቱ ሲገለጽ እንዴት ነው ይህ የእግዚአብሔር ሥራ ምንድን ነው ከሚል ደነገጥኩኝ፤ በዚያው ቅጽበት የተሰማኝ፣ እግዚአብሔር ይህን ታላቅ ሓላፊነት እንዴት እችለዋለሁ? በል አንተ ታውቃለህ፤›› የሚል እንደነበር አስረድተዋል፡፡
ከምርጫው ሦስት ቀናት በኋላ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በተከናወነው ሥርዐተ ሢመት÷ ለፓትርያርክነት መመረጣቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ጥሪ እንደኾነና ጥሪውን የተቀበሉት መኾኑን፣ መቀበላቸውም ለክብርና ለልዕልና ሳይኾን ለመሥዋዕት በመታዘዝ በመኾኑ የቅዱስ ሲኖዶሱን አባላት በመያዝ በጋራ እንደሚወጡት ያላቸውን እምነት ተናግረው ነበር፡፡
ፓትርያርኩ በዚያ ንግግራቸው ‹‹ቅዱስ ሲኖዶሱ በራሱ መተማመን አለበት›› ሲሉ በአጽንዖት የተናገሩ ሲኾን እንደ አንድ ልብ አሳቢ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾኖ በሥምረት ከሠራ፣ ችግር ይኖራል ብለው እንደማያምኑ ገልጸዋል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶሱ ሊሠሩ ይገባል በሚል ካሳወቋቸው ተግባራት መካከልም ቤተ ክርስቲያኒቱ ፍትሕ ርትዕ እኩልነት የሞላባት፣ መልካም አስተዳደር የሰፈነባት፣ የእውነትና የሐቅ መገኛ እንድትኾን በመንፈሳዊነት፣ ታማኝነትና ተጠያቂነት የተደገፈ መጠነ ሰፊ የሥራ እንቅስቃሴ ማድረግን ይጨምራል፡፡ ‹‹እምነትና ሐቅ በቤተ ክርስቲያን ካልተገኙ ከየት ይገኛሉ?›› ሲሉ የጠየቁት ፓትርያርኩ፤ ካህናትና ቤተ ክርስቲያኒቱን በሞያቸውና በልግሥናቸው አቅፈው ደግፈው የያዙ ምእመናንም የድርሻቸውን ለመወጣት ብርቱ ጥረት ማድረግ አለባቸው ማለታቸውም ይታወሳል፡፡
ከፕትርክና ሢመቱም በኋላ ለብዙኃን መገናኛዎች በሰጧቸው ቃለ ምልልሶች÷ ሰው ሊመሰገንም ሊሾምም፣ ሊሻርም፣ ሊወቀስም የሚገባው በጠባዩ፣ በግብረ ገብነቱ፣ በትምህርቱ ብቻ እየተመዘነ እንጂ በዘሩ አንወደውም አንጠላውም በማለት በቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ውስጥ ሥር የሰደደ የመጠቃቀሚያ መንገድ ነው የሚባለውን በጎሰኝነት መሳሳብን ተቃውመዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቷ ታላቅ መኾኗንና ለታላቅነቷ የሚመጥኑ ሰዎች መገኘት እንዳለባቸው በአጽንዖት የተናገሩት ፓትርያርኩ፣ ‹‹የተሟላና የተቃና ሥራ ለመሥራት ከኹሉ አስቀድሞ ብቃትና ጥራት ያለው ሥራ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ለዚኽ ደግሞ ሰው በሰው ላይ መደራረብ ሳይኾን ትምህርትና ችሎታ ያለው፣ ለተመደበበት የሥራ ደረጃ የሚመጥን ሰው መቀመጥ አለበት፤›› ብለዋል፡፡
የቤተ ክህነቱ አስተዳደር ከላይ እስከ ታች ተስተካክሎ የመልካም ሥራ አብነት ይኾን ዘንድ ‹‹ሙስና ይጥፋ፤ ተጠያቂነትና ሐቀኝነት ይስፋፋ›› የሚለውን ዐዋጅ ደጋግመው በማሰማት እየታወቁ የመጡት ፓትርያርኩ፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ስም ለመጠበቅና ክብርዋን ለመመለስ ሊወስዳቸው ይገባል ያሏቸውን የለውጥ ርምጃዎች በመዘርዝር በምልዓተ ጉባኤው አጀንዳነት አስይዘው ለማስወሰን አስችለዋል፡፡
ፓትርያርኩ ሥር ነቀል ለውጥን የሚያመጡና ቆራጥ አቋምን የሚሹ ናቸው ያሏቸው እኒህ ርምጃዎች÷ ብልሹ አሠራር በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ የሚታረምበትና የሚወገድበት፣ የአስተዳደር መዋቅሩና የሚሠራባቸው ደንቦች ሕጎች፣ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖረው ተደርጎ የሚሻሻልበት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ራእይና ተልእኮ በግልጽ የሚታይበት ስትራተጅያዊ የአመራር ሥርዐት የሚነደፍበት፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ላለው የገንዘብ አያያዝ አንድ ወጥ የኾነ ሥርዐት የሚዘረጋበት እንደኾነ አመልክተዋል፡፡
አቡነ ማትያስ አሳፋሪና አሳዛኝ ነው ያሉት የአሠራር ብልሽት ሳይታረም ቢቀጥል ቤተ ክርስቲያኒቱ ለሚገጥማት አስከፊ ችግር ፓትርያርኩ ራሳቸውን ከተወቃሾች ተርታ በመቁጠር ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚታደግና ችግሮቿን የሚቀርፍ አጀንዳ በመያዝ ‹‹በእግዚአብሔር፣ በታሪክና በመጪው ትውልድ ፊት›› የሚመዘን፣ ችግር ፈቺ ውሳኔ እንዲወሰን የቅዱስ ሲኖዶሱን አባላት አነሣስተዋል፡፡
ፓትርያርኩ ከሹመታቸው በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በርእሰ መንበርነት የመሩትና በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. የተካሔደው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በይፋ ባስታወቁት በዚህ መግለጫቸው ላይ በመወያየት፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ሥራዎቿን በመሪ ዕቅድ በመምራት፣ ሙስናንና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ ለመቅረፍ የሚያስችል ጥናት የሚያቀርብ ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቤተ ክህነቱ የሥራ ሓላፊዎችና ከምሁራን ምእመናን የተውጣጣ ዐቢይ ኮሚቴ ሠይሟል፡፡
ይኸው የቅ/ሲኖዶሱ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ የአደረጃጀትና አሠራር ጥናት የሁሉም አህጉረ ስብከት ማእከልና የመንበረ ፓትርያርኩ መቀመጫ በኾነው በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት እንዲደረግ መመሪያ ሰጥቷል፡፡ ሀ/ስብከቱም በመዋቅርና አደረጃጀት፣ በሰው ሀብት አስተዳደር፣ በሒሳብ አሠራርና ቁጥጥር የሚታይበትን የገዘፈና የተመሰቃቀለ ችግሩን ለመፍታት የባለሞያ ቡድን አቋቁሞ በፍጥነት ወደ ተግባር ገብቷል፡፡
በመንበረ ፓትርያርክም በአዲስ አበባ ደረጃም የተቋቋሙት ሁለቱም አካላት የጥናት ውጤታቸውን በጥቅምት ወር 2006 ዓ.ም. ለተካሔደው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ አቅርበው በማስገምገም የወሳኝ አካሉን ይኹንታ ከማግኘታቸውም በላይ ቀጣይ የአፈጻጸም አቅጣጫ ተሰጥቷቸዋል፤ የመሪ ዕቅድ ማህቀፉን ያስገመገመው ዐቢይ ኮሚቴ በቀጣይ ዕቅዱን በሥራ መተርጎም በሚያስችል ኹኔታ በዝርዝር አዘጋጅቶ እንዲያቀርብ መመሪያም ተሰጥቶታል፡፡
የአዲስ አበባውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ የሠራው የባለሞያ ቡድንም ጥናቱን ወደ ታች አውርዶ በካህናት፣ በምእመናንና በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በውይይት ካዳበረ በኋላ፣ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲያቀርብና በቋሚ ሲኖዶሱ እንዲጸድቅ በምልዓተ ጉባኤው በተሰጠው የአፈጻጸም አቅጣጫ መሠረት ተግባሩን አከናውኖ የብዙኃን ካህናትና ምእመናን ተቀባይነት ያረጋገጠውን የጥናት ሰነድ በሀ/ስብከቱ አማካይነት ለቅ/ሲኖዶሱ አስረክቧል፡፡
ከነገ በስቲያ ሰኞ፣ የካቲት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. በሚከበረው አንደኛ ዓመት የበዓለ ሢመት ዋዜማቸው ላይ የሚገኙት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በቀጣዩ የሥራ ዘመናቸው የተናገሯቸውንና ተጠንቶ የቀረበላቸውን በተግባር ለመተርጎም የሚንቀሳቀሱበት እንደሚኾን አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሓላፊዎች፣ አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ተስፋቸውን ገልፀዋል።
ቤተ ክህነቱ ያለበትን መሠረታዊ ተልእኮውን የማያገለግል የተንዛዛ ቢሮክራሲ፣ ወገንተኝነትና ሙስና በፓትርያርክ ደረጃ አምነውና ተቀብለው በዐደባባይ ገልጠው ለመናገር አቡነ ማትያስ የመጀመሪያው እንደኾኑ የሚናገሩት አንድ አገልጋይ፤ የፓትርያርኩ መግለጫዎች በየአጥቢያቸው ችግሩን የሚጋፈጡ ወገኖችን በልዩ ልዩ መንገድ እንዳነሣሣ ይህም ቢያንስ ብልሹ አሠራሩን ለሕገ ወጥ ጥቅም ያዋሉ አማሳኞችን እንዳሸማቀቀ ይገልጻሉ፡፡
ለዓመታት የተከማቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ዘርፈ ብዙ ችግር በአንድ ዓመት ተጠንቶ ሊታወቅ ይችል እንደኾነ እንጂ መፍትሔ ያገኛል ተብሎ እንደማይጠበቅ የጠቀሱት አገልጋዩ፤ አንድ ዓመት የፓትርያርኩን ስኬት ለመገምገም በቂ አይደለም ይላሉ፡፡ ፓትርያርኩ በጵጵስና ከተሾሙበት ጊዜ ጀምሮ በውጭ የነበሩ እንደመኾናቸው ቤተ ክህነቱን የመምራት ልምድ ሊያንሳቸው እንደሚችል ጠቁመው ይህን ክፍተት የሚጠቀሙ ከቀድሞም የነበሩና ዛሬም ያልታጠፉ የጥፋት እጆችን ተጽዕኖ በፓትርያርኩ ዙሪያ እንደሚያስተውሉ ገልጸዋል፡፡ ለዚህም ፓትርያርኩ የሚያስጠጓቸውን አማካሪዎች ማንነት በጥንቃቄ መለየት እንደሚኖርባቸው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ስለ ፓትርያርኩ የአንድ ዓመት ጉዞ የተጠየቁትና ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ከፍተኛ የሥራ ሓላፊ፣ ፓትርያርኩ ከተሾሙበት ዕለት አንሥቶ ያስተጋቧቸውን የተቋማዊ ለውጥ ዕሴቶችና መርሖዎች ተግባራዊ ለማድረግ ዙሪያቸውን መፈተሽ አለባቸው የሚለውን አስተያየት ይጋራሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያለው ኹኔታም ብቃት ያላቸውን እውነተኛ ባለሞያዎች ከፓትርያርኩ የሚያሸሽ እንጂ የሚያቀርብ አይደለም ብለዋል፡፡
የአስተዳደራዊ መዋቅር ማሻሻያ ሒደት የራሱ ተግዳሮቶች እንዳሉት የሚናገሩት የሥራ ሓላፊው፣ የአመራር ብቃትና ብስለት ተግዳሮቶቹን ለበጎ ለውጦ በመጠቀም እንደሚረጋገጥ ያስረዳሉ፡፡ ፓትርያርኩ ሥር ነቀልና ቆራጥ ተግባራዊ ርምጃ እወስዳለኹ ብለው በጀመሩት እንቅስቃሴ ተቃውሞ ሲገጥማቸው፣ ተቃውሞውን የማዳመጥ አባታዊ ሓላፊነት ቢኖርባቸውም ዋናውን የቅ/ሲኖዶሱን ውሳኔ ሳይቀር እስከማመቻመች መድረሳቸው የፀረ ሙስና አቋማቸው ከሚዲያ ፍጆታና ከንግግር ያላለፈ፣ የሚናገሩትንም ያህል ጠንካራና ጽኑ አቋም የሚይዙና ውሳኔ ሰጭ ናቸው ብለው እንዳያምኑ እንዳደረጋቸው አስረድተዋል፡፡ ይህም በውጤቱ የለውጥ ተቃዋሚዎቹን በማፈርጠምና የለውጥ ተስፋውን በማመንመን ሒደቱን አደጋ ውስጥ ሊከተውና የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር የበለጠ ሊያወሳስበው እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
ለፓትርያርኩ የአቋም ጽናት፣የሊቃነ ጳጳሳቱ የአቋም አንድነት አስፈላጊ ነው የሚሉት ሌላው አስተያየት ሰጪ፤ ከምንጊዜውም በላይ በቤተ ክህነቱ ላይ ተባብሶ የሚታየውን የተቋማዊ ለውጡን ሒደት የሚያደናቀፉ አላስፈላጊ ጣልቃ ገብነቶችን መቋቋምና የቅ/ሲኖዶሱን የውሳኔ ልዕልና ማስከበር እንደሚገባ ይመክራሉ፡፡
ፓትርያርኩ በተመረጡበት ቀን “እግዚአብሔር ይህን ታላቅ ሓላፊነት እንዴት እችለዋለሁ? በል አንተ ታውቃለህ›› ማለታቸው በርግጥም የሚገባ ነው ያሉት እኚሁ አስተያየት ሰጪ፤ ታላቋንና ጥንታዊቷን ቤተ ክርስትያን በአባትነት ለመምራት ተግዳሮቱ የበዛ ቢሆንም ወደ ዕድገትና ሥልጣኔ የሚያደርሰው ጎዳና በአቡነ ማትያስ ዘመነ ፕትርክና መጠረግና መደልደል ይገባዋል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡

Image

(አፈንዲ ሙተቂ)
———-
ኤርትራን በኢትኖግራፊ መነጽር በዳሰስኩበት የክፍል አንድ ጽሑፌ ላይ የተሰነዘሩ አንዳንድ አስተያየቶች የኤርትራን ችግር ከመሰረቱ እንዳስሰው አነሳስተውኛል፡፡ በተለይም ብዙዎች የሚሳሳቱባቸውን ነጥቦች ማብራራት ተገቢ ሆኖ ታይቶኛል፡፡ ስለዚህ በራሴ ጥናት በደረስኩበት መደምደሚያ መሰረት የግል እምነቴን የሚያንጸባርቀውን ይህንን መጣጥፍ አሰናድቻለሁ፡፡

====የኤርትራ ጥያቄ አነሳስ===

አንዳንዶች “የኤርትራ ጥያቄ በኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎች የተፈጠረ የስነ-ልቦና መቃወስ ነው” የሚል እይታ አላቸው፡፡ ይሁንና ይህ አነጋገር ከመሰረታዊ የታሪክ ሐቅ ጋር ይጋጫል፡፡ የኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎች ኤርትራን ለ60 ዓመታት ይዘዋታል፡፡ ይሁን እንጂ ህዝቡን የተለየ ስነ-ልቦና ያለው ህዝብ አድርገው ለመቅረጽ ብዙም አልሞከሩም፡፡ በሌላው የአፍሪቃ ሀገር እንደሚታየው ኤርትራዊያን ከጥንታዊ ማንነታቸው ብዙም አልተለወጡም፡፡ ባህላቸውንና ቋንቋቸውን በሚገባ አስጠብቀዋል፡፡ ለምሳሌ በኢጣሊያዊት ኤርትራ ጣሊያንኛ መናገር የሚችለው ህዝብ ከመቶ አስር እጅ ብቻ ነበር፡፡

የኤርትራ ጥያቄ መንቀልቀል የጀመረው በእንግሊዞች አስተዳደር ዘመን ነው፡፡ በዚያ ዘመን ፓርቲ፣ የሙያ ማህበራት፤ ነጻ ፕሬስ፣ ወዘተ በተግባር ላይ በመዋላቸው ህዝቡ በግዛቲቱ የወደፊት እጣ ላይ እንዲነጋገር መንገድ ከፍተዋል፡፡ ይህ ውይይት ተጧጡፎ ሁለት ተጻራራ ጎሳዎች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሆኗል፤- የአንድነትና የነጻነት ጎራ፡፡ ታዲያ የአንድነት ጎራው ዛሬ እንደሚባለው መላውን የኤርትራ ህዝብ የሚወክል አልነበረም፡፡ የነጻነት ደጋፊም ዛሬ እንደሚባለው በጣም አናሳ አይደለም፡፡ ከተባበሩት መንግሥታትና ከልዩ ልዩ ምንጮች የተገኙ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት 40% የሚሆነው የራቢጣ ኢስላሚያ ፓርቲ ደጋፊ እና 6 % የሚሆነው የሊበራል ፕሮግሬሲቭ ፓርቲ (የወልደአብ ወልደማሪያም ፓርቲ) ደጋፊ “ነጻነት”ን ይፈልጉ ነበር፡፡ የአንድነት ደጋፊዎች (የሀገር ፍቅር ማህበር አባላትና ሌሎቹም) ብዙሃን የነበሩ መሆናቸው ትክክል ቢሆንም ከኤርትራ ህዝብ 48 % የሚሆነውን ብቻ ነበር የሚወክሉት፡፡ የተቀረው አነስተኛ ቡድን ፕሮኢታሊያ (የጣሊያንን ሞግዚትነት የሚፈልግ ፓርቲ) ደጋፊዎች ነበሩ (እነዚህኛዎቹ ከኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎች የተወለዱ ክልሶቸ ነበሩ)፡፡

የኤርትራን ጥያቄ ከዐረቦች ተንኮልም ከእስልምና ተስፋፊነት ጋር ማያያዝም አግባብ አይደለም፡፡ ጥያቄው በኤርትራ ምድር ነው የተነሳው እንጂ በዐረቦች ዘንድ አይደለም፡፡ ዐረቦች ከጥንት ጀምሮ ሁለታችንንም “ሐበሻ” ነው የሚሉን፡፡ በ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ኤርትራን ለመያዝ የዘመተችው ግብጽ ፍላጎቷ ሁሉንም የሰሜን ምስራቅ አፍሪቃ ሀገራት ጠቅላላ በመያዝ የአባይን ምንጭና የቀይ ባህር ንግድን መቆጣጠር እንጂ ኤርትራን ለብቻ ገንጥላ የተለየ ቀጣና ማድረግ አልነበረም፡፡ ለዚህም ነበር ግማሽ ጦሯን ይዛ ከዘይላ እስከ ሀረር ድረስ የተዘረጋ ግዛት የመሰረተችው፡፡ በኤርትራ በኩል ግን ከምጽዋ በስተቀር ሊሳካላት አልቻለም፡፡ በራስ አሉላ የሚመራው ጦር ድባቅ እየመታት መልሶአታል፡፡ በታጁራና ጅቡቲ በኩል የመጣውን ጦሯን (በኮሎኔል ሙዚንገር የሚመራውን) ደግሞ የአፋር ጀግኖች ደምስሰውታል፡፡

በእንግሊዞቹ ዘመን የነጻነቱን ጥያቄ በስፋት ይደግፉ የነበሩት ሙስሊሞች እንደነበሩ መካድ አይቻልም፡፡ ሙስሊሞቹ ይህንን ሃሳብ ሲያቀነቅኑ የነበሩት በዘመኑ በኢትዮጵያ ውስጥ ይታይ ከነበረው ተጨባጭ እውነታ በመነሳት እንጂ “ኢትዮጵያ የምትባለውን ሀገር ስለሚጠሉት አይደለም፡፡ የኤርትራዊያኑ ሙስሊሞች ስጋት “በኃይለ ሥላሤዋ ኢትዮጵያ ውስጥ ከተቀላቀልን በሀይማኖታችን ምክንያት ከፍተኛ ጭቆና ይፈጸምብናል፤ ስለዚህ ኤርትራ ነጻ ሀገር ብትሆን ነው መብታችን የሚከበረው” የሚል ነው፡፡ የአጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት የሙስሊሞቹን ስጋት ለመቅረፍ የሚያስችሉ እርምጃዎችን ቢወስድ ኖሮ የኤርትራ ጥያቄ ባልተከሰተ ነበር፡፡

ከላይ እንደተጠቀሰው ሁለቱ ጎራዎች ተቀራራቢ ሚዛን ነው የነበራቸው፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ኤርትራ በፌዴሬሽን ከኢትዮጵያ ጋር እንድትተሳሰር ያደረገበት አንዱ ምክንያትም የሁለቱ ጎራ ደጋፊዎች የተቀራረበ የሀይል ሚዛን (46ለ48) ያላቸው መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው፡፡ በሌላ በኩል በእንግሊዞች አስተዳደር የመጨረሻ ዓመታት በሁለቱ ጎራዎች መካከል ከፍተኛ የሆነ ሽኩቻና መጠፋፋት ይካሄድ ስለነበር የተባበሩት መንግሥታት የትኛውንም ጎራ ደግፎ ጥያቄውን ቢፈታው የከረረ የርስ በርስ ጦርነት ይከሰታል የሚል ፍርሃት አድሮበት ነበር፡፡ በመሆኑም “ኤርትራ በፌዴሬሽኑ ከኢትዮጵያ ጋር ብትዋሃድ በሁለቱም ጎራ መካከል ፍጅት እንዳይቀሰቀስ ለማገዝ ይችላል” የሚል እምነት ነበረው፡፡

=====የፌደሬሽኑ ፎርሙላ====

ይህኛውም ብዙ ሰዎች የሚሳሳቱበት ነጥብ ነው፡፡ የኃይለ ሥላሤ መንግሥትም ሆኑ የደርግ መንግሥት ደጋፊዎች ለኤርትራ የተፈቀደው ፌዴሬሽን ምን ዓይነት እንደሆነ ግንዛቤው ያላቸው አይመስለኝም፡፡ “ፌዴሬሽኑ መነካት አልነበረበትም” የሚል ሐሳብ ሲሰነዘር ለተቃውሞ የሚነሱትም በዚሁ ምክንያት ይመስለኛል፡፡ በሌላ በኩል የነጻነት ጎራ ደጋፊዎች በተባበሩት መንግሥታት የተፈቀደውን የፌዴሬሽኑን ፎርሙላ ከከፍተኛ ቅሬታ ጋር የተቀበሉት መሆናቸውም ይረሳል፡፡

ለኤርትራ የተፈቀደው ፌዴሬሽን ዛሬ ላይ ተሁኖ ሲታይ እጅግ በጣም “ሊበራል” የሚባል ነበር፡፡ ሌሎች የኢትዮጵያ ግዛቶችም በዚያ ሞዴል ቢቀረጹ ኖሮ ዛሬ የሚታየው ምስቅልቅል ሁኔታ ተለውጦ ሀገራችን ሌላ መልክ በያዘች ነበር፡፡ በዚያ ዘመን ነጻ ያልወጡት ሶማሊላንድና ጅቡቲም የኛ አካላት ሊሆኑ ይችሉ ነበር ለማለትም ያስደፍራል፡፡ ነገር ግን ንጉሡና ባለሟሎቻቸው በግዴለሽነት ሰረዙት፡፡
——
ኤርትራ በወቅቱ ከኢትዮጵያ ጋር የተዋሃደችበት ፌዴሬሽን በትክክለኛው አገላለጽ ሲታይ “ሙሉ ራስ ገዝ አስተዳደር” የሚባል ነው፡፡ ኤርትራ የራሷ ፓርላማ፣ ህግ አስፈጻሚና ህግ ተርጓሚ አካላት አሏት፡፡ መንግሥቱን የሚመራው “ዋና ስራ አስፈጻሚ” (Chief Executive officer) በፈረቃ ከክርስቲያን ደገኞቹና ከሙስሊም ቆለኞቹ እንዲመረጥ ተወስኗል፡፡ ዋና ስራ አስፈጻሚው ክርስቲያን ከሆነ የፓርላማው ፕሬዚዳንት ከሙስሊም ቆለኞች ነው፡፡ ስራ አስፈጻሚው ከቆለኞቹ ሲመረጥ ደግሞ የፓርላማው ፕሬዚዳንት ከደገኞች ይሆናል፡፡

የኤርትራው ራስ ገዝ አስተዳደር ከውጭ ጉዳዮች፣ ከገንዘብ ነክ ጉዳዮች፣ ከንግድና ከመገናኛ በስተቀር በሁሉም ነገሮች ላይ መወሰን ይችላል፡፡ እነዚህ አራት ዘርፎች የሚመሩት የፌዴራሉ መንግሥት ሆኖ በሚሰራው የአጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት ነው፡፡ የምጽዋና የአሰብ ወደቦችም በፌዴራሉ መንግሥት ስር ነበር የሚተዳደሩት፡፡
—-
ታዲያ ይህ ፌዴሬሽን ምን በደለ?. ምን አጠፋ?… ይህንን ፌዴሬሽን ለማፍረስ መቸኮል አግባብ ነው?…. ዛሬ እኮ ለኢትዮጵያ እንዲህ ዓይነት ያልተማከለ አስተዳደር ያስፈልጋታል ነው እያልን ያለነው፡፡ የአጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት ግን በማን አለብኝነት አጠፋውና ረዥሙን ጦርነት ቀሰቀሰ፡፡ የሀገራችንም ታሪክ ሌላ መልክ ያዘ፡፡

===ፌዴሬሽኑ እንዴት ፈረሰ?====

ሌላው በብዙ ሰዎች የሚሰነዘረው አባባል “ፌዴሬሽኑ የፈረሰው በአንድነት ኃይሎች ሙሉ ፈቃደኝነትና ግፊት ነው” ይላሉ፡፡ ይህኛውም አባባል ምንም ማስረጃ የለውም፡፡ እንዲያውም በፌዴሬሽኑ ዘመን የፌዴሬሽኑ አስተዳዳሪዎች ይከተሉት ከነበረው አድሎአዊነት የተነሳ ከአንድነት ጎራ ደጋፊዎች መካከል እጅግ የሚበዙት የፌደሬሽኑ ተቃዋሚ በመሆን የነጻነቱን ጎራ ተቀላቅለዋል፡፡ በተጨማሪም የቢትወደድ አስፋሓ መንግሥት በኤርትራ ሰራተኞችና የሙያ ማህበራት ላይ በሚያካሄዳቸው የእመቃ ተግባራት ብዙዎችን አስቀይሟል፡፡ ስለዚህ የአንድነት ሀይሎች ጉልበት ኖሯቸው በመንግሥቱ ላይ ግፊት የሚፈጥሩበት ሁኔታ በጭራሽ አልነበረም፡፡ አብዛኛው የኤርትራ ህዝብ “አደይ ኤሪትሪያ”ን መዘመር የጀመረው በነዚያ አመታት ነው፡፡

ፈዴሬሽኑን በግልጽ ያፈረሱት የቢትወደድ አስፋሓ ደጋፊችና ጄኔራል አቢይ አበበን የመሳሰሉ የአጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት ሹማምንት ናቸው፡፡ ቢትወደድ አስፋሓ ከመጀመሪያኑ በኤርትራ የተሾሙት ለዚሁ ነበር፡፡ እኝህ ሰው በኤርትራ ተወለዱ እንጂ አልኖሩባትም፡፡ ዕድሜአቸውን ያሳለፉት እዚሁ ኢትዮጵያ ውስጥ በትርጉም ስራ ላይ ነበር፡፡ በጣሊያን ወረራ ዘመን በአዲስ አበባ ሀገረ ገዥነት ተሹመው በአዲስ አበባ ገነተ-ልዑል ቤተ መንግሥት የሚቀመጡት የዱክ ኦፍ አኦስታ እና የጄኔራል ናዚ አስተርጓሚ ነበሩ፡፡ በኋላም በሲቪል ሰርቪሱ ውስጥ ከፍተኛ ስልጣን ተሰጥቷቸዋል፡፡ ለጣሊያን መንግሥት በአስተዳዳሪነት ተሹመው ለሰጡት አገልግሎት ቤኒቶ ሙሶሎኒ ፊት ቀርበው የፈረሰኛ ኒሻን ተሸልመዋል (አምባሳደር ዘውዴ ረታ፣ የኤርትራ ጉዳይ፣ ገጽ 461-462 ተመልከቱ)፡፡

ቢትወደድ አስፋሓ ለሶስት ዓመታት በኤርትራ ፌዴሬሽን የንጉሠ ነገሥቱ ምክትል እንደራሴ ነበሩ፡፡ በዚያ ዘመን በደጃች ተድላ ባይሩ የሚመራው የኤርትራ አስተዳደር በሁለት እግሩ ቆሞ እንዳይሰራ በማድረግ ተግባር ላይ ነው የተጠመዱት፡፡ በዚህ ረገድ ከዋናው እንደራሴ ራስ አንዳርጋቸው መሳይ (ሁለተኛው የልዕልት ተናኘወርቅ ባለቤት) ጋርም ዘወትር ይወዛገቡ ነበር፡፡ የሚገርመው ነገር አጼ ኃይለ ሥላሤ አማቻቸው በቢትወደድ አስፋሓ ላይ የሚያቀርቡትን ክስ በስራ ከመበለጥ የመጣ የዝቅተኝነት ስሜት (inferiority complex) አድርገው መቁጠራቸው ነው፡፡

ቢትወደድ አስፋሓ ከ1955 ጀምሮ ፌደሬሽኑ እስከፈረሰበት ድረስ (1962) ቺፍ ኤክስኩቲቭ ኦፊሰር ወይንም የራስ ገዙ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆነው ሰርተዋል፡፡ እዚህ ላይ አንድ ነገር ልብ በሉ፡፡ የኤርትራን ዋና አስፈጻሚ የሚመርጠው የኤርትራ ፓርላማ ነው፡፡ ተመራጩ የፓርላማው አባል መሆን አለበት፡፡ ይሁንና የአጼ ኃይለ ሥላሤ “የኤርትራ ስራ አስፈጻሚ የግዴታ የፓርላማው አባል መሆን የለበትም” በሚል የጉልበተኝነት ስሜት ቢትወደድ አስፋሓ ለፌዴሬሽኑ ስራ አስፈጻሚነት እንዲመረጡ አድርገዋል፡፡

ቢትወደድ አስፋሓ የኤርትራ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆነው ሲሾሙ መጀመሪያ ያደረጉት ነገር ለሚወስዷቸው እርምጃዎች ህጋዊ ሽፋን ለማሰጠት የኤርትራ ፓርላማ የኃይለ ሥላሤ መንግሥት እንደሚፈልገው አድርጎ ማዋቀር ነው፡፡ በዚህም መሰረት ቀደም ሲል በተባበሩት መንግሥታት ታዛቢነት የሚካሄደውን የምርጫ ዘይቤ ለወጥ በማድረግ አሁን በአፍሪካ የሚካሄደውን የምርጫ ቲያትር አመጡ፡፡ ለምሳሌ ከምዕራብ ቆላ በሚመረጡ ሙስሊሞች ወንበሮች ላይ ለርሳቸው ታማኝ የሆኑትን የደጋ ሙስሊሞችን አስመርጠዋል፡፡

ከዚህ በኋላ ነበር ፌዴሬሽኑን የማፈራረሱ ስራ የተጀመረው፡፡ ፓርቲዎች ታገዱ፡፡ ነጻ ፕሬስም ታገደ፡፡ የሰራተኛ ማህበራትም ታገዱ፡፡ “ዐረብኛ የባዕድ ቋንቋ ነው” በሚል ከህገ-መንግሥቱ ተፍቆ ወጣ፡፡ ከዚያም የኤርትራ ባንዲራ እንዳይውለበለብ ተደረገ፡፡ በማስከተልም ትግርኛ ከስራ ቋንቋነት ተሰረዘ፡፡ በምትኩ አማርኛ የስራ ቋንቋ ሆነ፡፡ “ዋና ስራ አስፈጻሚ” የሚለው የፌዴሬሽኑ ገዥ መጠሪያም “ዋና አስተዳዳሪ” በሚል ተተካ፡፡ ፡ በመጨረሻ ላይ “የኤርትራ ፓርላማ ወስኗል” በሚል ፌዴሬሽኑ ፈረሰ፡፡

ፌዴሬሽኑ እንዲህ እየተገዘገዘ ነበር ቀስበቀስ የፈረሰው፡፡ የፈዴሬሽኑ አፍራሾችም ድሮ ለአንድነት የታገሉ የአንድነት ሀይሎች ሳይሆኑ ቢትወደድ አስፋሓ በሚፈልጉት መንገድ የተመረጡ አድር ባዮች ነበሩ፡፡

ይህንን የቢትወደድ አስፋሓን ታሪክና የማምታት ዘዴ ብዙዎች ጽፈውታል፡፡ በአማርኛ ታሪኩን በሰፊው የጻፉት ግን አምባሳደር ዘውዴ ረታ ናቸው፡፡ አምባሳደር ዘውዴ መጽሐፉን ሲጽፉ ቢትወደድ አስፋሓን የአንድነትና የነፃነት ጠበቃ በማድረግ ነው የሚያንቆለጳጵሱት፡፡ ቢትወደድ አስፋሓ የወሰዱትን እርምጃ አንድ በአንድ እየተረኩልን እንኳ ህገ-ወጥነታቸውን ያደንቁላቸዋል፡፡ ታዲያ በጣም የሚያሳዝነው ነገር በዚሁ መጽሐፍ ውስጥ ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ኤርትራን በፌዴሬሽን ለማስመለስ ያደረጉት እልህ አስጨራሽ ትግልና ፌዴሬሽኑ እንዳይፈርስ ያደረጉት ጥረት ሰፋ ብሎ የቀረበ መሆኑ ነው፡፡ ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ለአጼ ኃይለ ሥላሤ “በህግ ፈርመን የተቀበልነውን አደራ ማክበር አለብን” የሚል ተደጋጋሚ ምክር ቢሰጧቸውም ንጉሡ በጭራሽ ሊሰሟቸው አልፈቀዱም፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያና ኤርትራ ሁለት ሀገር የመሆናቸው እርሾ ተጠነሰሰ፡፡

===የኤርትራ ነጻነት ትግል እና የኤርትራዊነት ስነ-ልቦና===

የኤርትራ ነጻነት ትግል የተለኮሰው ፌዴሬሽኑ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ታዛቢዎች በወጣለት ህገ-መንግሥት መሰረት ስራዎቹን በአግባቡ ማከናወን ስላቃተው ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጸው በ1950ዎቹ አጋማሽ አብዛኛው ህዝብ ከአንድነት አቀንቃኝነት ወጥቶ ወደ ነጻነት ፈላጊው ጎራ መቀላቀል ጀምሯል፡፡ ትግሉን በተደራጀ መንገድ የመጠንሰሱን ሃሳብ የወጠነው ግን ሰባት ሰዎች የመሰረቱት “ማህበር ሸውአተ” የሚባለው እድር መሳይ ማህበር ነው፡፡ ይህ ማህበር ከጥቂት ጊዜ በኋላ “ምንቕስቓስ ሓርነት ኤርትራ” (“ሐረካት ታሕሪረል ኤሪትሪያ”/Eritrean Liberation Movement) የሚባል ድርጅት ወለደ (ድርጅቱ በታሪክ ምዕራፎች “ሐረካ” እየተባለ ነው የሚጠራው)፡፡

“ሐረካ” ወደ ትግሉ የገባው ፌዴሬሽኑ ከመፍረሱ ከሶስት ዓመታት አስቀድሞ ነው፡፡ የትግሉ ዋነኛ ዓላማም “የኤርትራ ፌዴሬሽን በህገ-መንግሥቱ መሰረት ስራውን እንዲያከናውን መጠየቅ” ነበር፡፡ ይሁንና አብዛኛው ኤርትራዊ ኤሊት ለአስር ዓመታት ባየው የፌዴሬሽኑ አሰራር ተስፋ የቆረጠ በመሆኑ “የፌዴሬሽን አሰራርን በጭራሽ አንቀበልም” ባይ ሆነ፡፡ በተለይም የቀድሞ የኤርትራ ፓርላማ አባላት በዚህ ላይ ግትር አቋም ያዙ፡፡ በመሆኑም ከነጻነት በመለስ ሌላ አማራጭ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነው “ተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ” ወይንም “ጀብሃት ታሕሪረል ኤሪቲሪያ” (ጀብሃ) እ.ኤ.አ መስከረም ወር 1961 በካይሮ ከተማ ብዙ ህዝብ በተሰበሰበት ተመሰረተ፡፡ ጀብሃ ትግሉን ለሃያ ዓመታት ከቀጠለበት በኋላ በውስጣዊና ውጫዊ ችግሮች ተዳክሞ ሲወድቅ ከርሱ የተገነጠለው “ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ” ወይንም “ጀብሃት አሽ-ሻዕቢያ ሊ-ተሕሪረል ኤሪቲሪያ” (ሻዕቢያ) እርሱን ተክቶ መዋጋቱን ተያያዘው፡፡ በ1983 (1991) ኤርትራ ነጻ ሀገር ሆነች ፡፡ የኤርትራ የነጻነት ትግል የተጓዘበት መንገድ ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡ ይህ መሆኑ እየታወቀ “የቅኝ ገዥዎች ተንኮል”፣ “የዐረቦች ሸር” ወዘተ.. የሚሉ ሰበቦችን መደርደር ራስን መደለል ነው፡፡

ኤርትራዊነት “የቅኝ ተገዥነት ስሜት የፈጠረው የተቃወሰ ስነ-ልቦና ነው” የሚለውም ክስ ከዚሁ ጋር ነው የሚታየው፡፡ ኤርትራዊያንን እስከምናውቃቸው ድረስ ለፈረንጅ ገዥ ያላቸው ስሜት ከኛ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ለዚህም ነበር በ1929-1933 የኢጣሊያ ወረራ ዘመን በርካታ የኤርትራ ጀግኖች ድንበር አቋርጠው ከኢትዮጵያ አርበኞች ጋር የተቀላቀሉት፡፡ የኢትዮጵያ ባንዲራ በኢጣሊያ ወታደሮች መረገጡ አንገብግቦት የጠላቶቹን አንገት በሰይፍ የቀላው ጀግናው ዘርዓይ ደረስ ከተወለደበት ኤርትራ ውጪ የተቀረውን የኢትዮጵያ ክልል ለአንድም ቀን ረግጦ አያውቅም፡፡ ጀግኖቹ አብረሃ ደቦችና ሞገስ አስገዶምም በቅኝ ገዥዋ ኮሎኒያል ኤሪትሪያ ነበር የተወለዱት፡፡ የህዝቡ ስነ-ልቦና በቅዥ ተገዥነት ስሜት የተቃወሰ ቢሆን ኖሮ እንደዚህ የበረከቱ ጀግኖች በሀገሩ ላይ ባልበቀሉ ነበር፡፡
——
ለኤርትራ ጥያቄ መፈጠር እርሾ የሆነው የቅኝ ተገዥነት ስሜት ሳይሆን የኛ መንግሥታት ሲያካሄዱት የነበረው ኢ-ፍትሐዊነትና ብሄራዊ ጭቆና ነበር፡፡ ያለፉት መንግሥታት ቤታችንን በማስተካከል ለሁላችንም እንዲመች ቢያደርጉት ኖሮ ጥያቄው ባልተፈጠረ ነበር፡፡ ለዚህ ፋና ወጊ የነበረውን የልጅ እያሱ ፖሊሲ መጥቀስ ይቻላል፡፡

ይልቅ ከኤርትራዊያን ጋር የማንግባባው “ኢትዮጵያ ቅኝ ገዥ ነበረች” በሚለው አገላለጽ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ቀርቶ ረጅም ሀገር አቋርጠው ምጽዋን ለአራት መቶ ዓመታት የያዙት ኦቶማን ቱርኮች እንኳ ቅኝ ገዥ ተብለው አልተጠሩም፡፡ መንግሥታቶቻችን የኤርትራን ጥያቄ ጆሮ ዳባ ልበስ ብለው ለመስማት ባይፈለጉትም አውሮጳዊያን እንዳደረጉት አዲስ ሀገር በወረራ አልያዙም፡፡ መሬቱ ከጣሊያኖች መምጣት በፊት በራስ አሉላ ስር “መረብ ምላሽ” ተብሎ ይተዳደር ነበር፡፡ በጥንቱ ታሪክ ውስጥ ደግሞ ኤርትራ “ባህረ ነጋሽ” የሚል ስያሜ የነበራት ዋነኛዋ የኢትዮጵያ አስኳል እንደነበረች ነው የምናውቀው፡፡ የጥንቱ “አቢሲኒያ” (ሐበሻ) የሚለው አጠራር መጀመሪያ የተፈጠረው በኤርትራና በትግራይ ውስጥ ነው፡፡ እዚህ ላይ ፕሮፌሰር መስፍን በግንቦት ወር 1983 የለንደን ኮንፈረንስ ሲካሄድ ለፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ “እኛ ኢትዮጵያዊያን አይደለንም ማለታችሁ ትልቁ ስህተታችሁ ነው፤ ኢትዮጵያዊያን እኛ እንጂ ሌሎች አይደሉም ብትሉ ኖሮ ትንሽ እውነት ይኖርበት ነበር” ያሉትን መጥቀስ ተገቢ ነው፡፡ የፕሮፌሰር መስፍን አገላለጽ ለዘመናችን ሰው ባይስማማም የታሪክ ሐቅ አለበት፡፡

====የመንግሥታቱ የቅራኔ አፈታት እንከኖች====

የኤርትራን ጥያቄ ያወሳሰበው አንዱ ምክንያት መንግሥታቱ ቅራኔዎችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት አለመከጀላቸው ነው፡፡ ሁሉም ሀገረ ገዥ እና አስተዳዳሪ ጦርኝነትን እንጂ ተስፈኝነትን ሲዘምር አልታየም፡፡ እስቲ ነገሮችን በምሳሌ ላስረዳ፡፡

ጀብሃ በአንድ ጊዜ ብዙ ተከታዮችን ለማፍራት የቻለው ራስ አስራተ ካሣ በሚያካሄዱት የጭካኔ ዘመቻ የኤርትራ ቆላ ህዝብ በብዛት ወደ ግንባሩ በመጉረፉ ነው፡፡ ራስ አስራተ ከሚወስዱት እርምጃ ሳይታረሙ ተከታታይ ዘመቻዎችን ሲያካሄዱ ደግም ህዝቡ በብዛት ወደ ሱዳን ተሰደደ፡፡ የተቀረው ጀብሃን ተቀላቀለ፡፡ ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርስ “ሬድ ቲርስ” በተሰኘው መጽሓፋቸው ራስ አስራተ ያዘመቱት ጦር በወሰደው እርምጃ በአንድ ጀንበር ብቻ ከአምስት ሺሕ የማያንስ ህዝብ ማለቁን ያስረዳሉ፡፡

የደርግ መንግሥት ሲመጣም ችግሩ ተባባሰ እንጂ አልተቃለለም፡፡ በተለይም ሻዕቢያ ተከታታይ ድል በሚቀዳጅባቸው የመጨረሻዎቹ ዓመታት ሺዎች በታንክና በመድፍ አልቀዋል፡፡ ለምሳሌም በዓለም የመገናኛ ብዙሃን ሰፊ የመነጋገሪያ አጀንዳ ለመሆን የበቃውንና በ1980 በቀይ ባህር ዳርቻ ባለችው የሸዒብ ከተማ ህዝብ ላይ የደረሰውን ፍጅት መጥቀስ ይቻላል፡፡

እነዚህ መንግሥታት የኤርትራን ችግር በሰላም ለመፍታት የወሰዷቸው እርምጃዎች ኢሚንት ናቸው፡፡ ራስ አስራተና የአሜሪካ ሚሊታሪ አዛዦች በአጼ ኃይለ ሥላሤ ጠያቂነት የተቋቋመውን የሰላም ኮሚቴ በመጥለፍ ጀብሃና ሻዕቢያ እንዲጨራረሱ ለማድረግ ሞከሩ፡፡ የደርግ መንግሥት ደግሞ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ የክፍለ ሀገሩን ችግር በሰላም ለመፍታት ያግዛሉ በማለት ተስፋ ያሳደረባቸውን ጄኔራል አማን አንዶምን አስገደለ፡፡ እንዲህ ማድረጋቸው ሳያንስ በጄኔራል አማን ላይ ተከታታይ የቅጥፈት ወሬ ማስወራት! ያሳዝናል፡፡

ደርጎች እስከዛሬ ድረስ “ጀኔራል አማን የተገደሉት ወንበዴዎቹ ኤርትራን እንዲገነጥሉ ሁኔታዎችን ማመቻቸታቸው ስለተደረሰበት በዚህ አኩርፈው ቤታቸው ውስጥ ስለመሸጉ ነው” ይላሉ፡፡ በደርግ ወገን ሆነው የጻፈ የትኛውም ሰው ይህችን ቃል ይደጋግማል፡፡ ይሁንና ለህሊናቸው ታማኝ የሆኑት ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም “በጄኔራል አማን ላይ የተደረገው ቅጥፈት እጅግ በጣማ ያሳዝናል፤ ጄኔራል አማን ኤርትራ ከኢትዮጵያ እንዳትገነጠል ተገቢውን ጥረት ያደረጉ ኩሩ ኢትዮጵያዊ ናቸው” በማለት ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል (የክህደት ቁልቁለት የተሰኘውን መጽሐፍ አንብቡ)፡፡ ጄኔራል ጃጋማ ኬሎም በሰጡት የምስክርነት ቃል ይህንኑ አረጋግጠዋል፡፡

የደርግ መንግሥት የሚወስዳቸው እርምጃዎች የኤርትራ ጥያቄ እጅግ በጣም የተወሳሰበ እንዲሆን ነው ያደረጉት፡፡ ደርግ በመውደቂያው ሰሞን ከሻዕቢያ ጋር ንግግር ለማድረግ መሞከሩ ሚዛን የሚደፋ ዜና ለመሆን ያልቻለው ወርቃማው እድል ካመለጠ በኋላ የተመዘዘ ካርድ ስለሆነ ነው፡፡

ከደርግ ቀጥሎ የመጣው ህወሐት ለኤርትራ ጥያቄ እውቅና መስጠቱ የሚያስወድሰው ነው፡፡ ነገር ግን ከኤርትራዊው አጋር ድርጅቱ (ሻዕቢያ) ጋር ወደፊት አብሮ መኖር ስለሚቻልበት ሁኔታ በመነጋገር የኢትዮጵያን ጥቅም የሚያሰፋበትን ሁኔታ መቀየስ ሲገባው “የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው” የሚል ግትር አቋም የሚያራምድ ሆኖ ተገኘና ህዝቡን አስቀየመ፡፡ በተጨማሪም የኤርትራ ሪፈረንደም በተካሄደበት ወቅት ውሳኔውን የሚያጸድቅበት “ማንዴት” ከህዝብ ያልተሰጠው የሽግግር ጊዜ መንግሥት ይዞ ውሳኔውን በማጽደቁ የህዝቡን ልብ ሰበረው፡፡ ለዚህችው ብቻ ሲታገል የኖረ አስመሰለበት፡፡
——–
ከላይ እንደለገጽኩት የኤርትራ ጥያቄ አግባብነት የነበረው ጥያቄ ነው፡፡ መንግሥታቱ ግን በተገቢው መንገድ አላስተናገዱትም፡፡ ኃይለ ሥላሤና ደርግ በጀብደኝነት ጥያቄውን ረገጡት፡፡ ይህኛው መንግሥት ደግሞ ከህዝብ ስል&

By Addis Admass Newspaper , Written by Administrator

Image

ኪሳራው በጊዜ ሲሰላ፣ የአገሪቱን የስልጣኔ ጭላንጭል ያዳፈነ፣ የ30 ዓመት የኋሊት ጉዞ ነው።
30 ዓመት ቀላል አይደለም፤ እነ ደቡብ ኮሪያ ከድህነት ወደ ብልፅግና የተሸጋገሩበት ጊዜ ነው።
“የአብዮተኛው ትውልድ”ን ኪሳራዎችን ለመደበቅ ተብሎ ብዙ ታሪክ ተድበስብሷል
ትምህርት የተስፋፋው፣ የሴት ተማሪዎች ቁጥር ያደገው ከአብዮቱ በፊት ነው ወይስ በኋላ?
የኤሌክትሪክ፣ የስልክ፣ የመንገድና የአየር ትራንስፖርት በፍጥነት የተሻሻለውስ መቼ ነው?
በእህል ምርት፣ በኢንዱስትሪ፣ በኤክስፖርት መስኮች የብልፅግና ምልክት የታየውና የጠፋውስ?
የሙያ ፍቅር ያበበው፤ ስነፅሁፍ፣ ትያትርና ሙዚቃ ያደገው፤ ስፖርት የተሻሻለው መቼ ይሆን?

በ1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ፣ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የመጡ የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ላይ የዳሰሳ ጥናት ያካሄዱት ዊሊያም ሻክ፤ በአገሪቱ እያቆጠቆጠ ከመጣው የትምህርትና የስልጣኔ ጅምር ጋር መልካም የአስተሳሰብ ለውጥ እየመጣ እንደነበር ይገልፃሉ። አንደኛ፤ የዘመኑ ወጣቶች እንደ ጥንቱ የመንግስት ስልጣንንና ተቀጣሪነትን አልያም የሃይማኖት መሪነትንና ሰባኪነትን የሚመኙ አይደሉም። ሁለተኛ፤ “ይሄኛው ሙያና ይሄኛው የሕይወት ዘይቤ፣ ለአማራ፣ ለኦሮሞ ወይም ለሶማሌ ተወላጅ ነው። ያኛው ሙያና ያኛው የኑሮ ዘይቤ ደግሞ ለትግራይ፣ ለወላይታ ወይም ለጉራጌ ተወላጅ ነው” የሚሉ የዘልማድ አዝማሚያዎችን አይቀበሉም። የ1950ዎቹ ወጣቶች የሙያና የግል ሕይወታቸውን በራሳቸው መንገድ መምራት እንደሚችሉ የሚያምኑ ሆነዋል።
ተማሪዎቹ ከተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የመጡ ቢሆኑም፤ የሙያ ምርጫቸው ይመሳሰላል። ከመንግስት ስልጣንና ተቀጣሪነት ወይም ከሃይማኖት ሰባኪነት ይልቅ፤ ከሁሉም በላይ ቅድሚያ የሚሰጡት ለምህንድስና ወይም ለህክምና ሙያ፣ ለሜካኒክነት ወይም ለአስተማሪነት ሙያ እንደሆነ ጥናቱ ገልጿል። በአጭሩ፤ በያኔው የስልጣኔ ጭላንጭል፤ ለእውቀትና ለሳይንስ፤ ለሙያዊና ለምርታማ ስራ ክብር የሚሰጥ ትውልድ እየተፈጠረ ነበር። በአገሪቱ እየታየ የነበረውንም የትምህርትና የኢኮኖሚ ብሩህ አቅጣጫ ያመላክታል። Occupational Prestige, Status, and Social Change in Modern Ethiopia: William A. ShackSource: Africa: Journal of the International African Institute, Vol. 46, No. 2 (1976), pp. 166-181
በ1950ዎቹ ዓ.ም ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች ከእንቅልፏ እየነቃች እንደነበረ የሚያሳዩ የጥበብ ስራዎችንም መጥቀስ ይቻላል። የሃዲስ አለማየሁና የፀጋዬ ገብረመድህን ድርሰቶች፣ የነጥላሁን ገሠሠና የነምኒልክ ወስናቸው የሙዚቃ ስራዎች፣ ዛሬ ከአርባ እና ሃምሳ አመታት በኋላም፣ ወደር አልተገኘላቸውም። በእግር ኳስ እና በሩጫ ስፖርቶችም እንዲሁ።
በመንግስት አስተዳደር በኩልም፤ ትልቅ “የስልጣኔ አብዮት” የተካሄደው፣ ከ1960ዎቹ “አብዮተኛ ትውልድ” በፊት ነው። ለሺ አመታት በሃይማኖታዊ ሰነዶች (በክብረ ነገስትንና በፍትሃ ነገስት) ላይ ተመስርቶ የቆየውን የአገሪቱ ሥርዓትና ሕግ፣ ከኋላቀርነት ለማላቀቅና የስልጣኔ እድል ለመፍጠር ያስችላሉ የተባሉ የሕገመንግስት እና የምርጫ ህጎች ከ1923 እስከ 1948 ዓ.ም ፀድቀዋል። የተለያዩ የፍትሐ ብሄርና የወንጀል ሕጎች ከ1935 እስከ 1960ዎቹ መግቢያ ድረስ ታውጀዋል። የወንጀልና የፍትሐ ብሄር ህጎቹ እስከ ዛሬ ድረስ ይሰራሉ – (በ2000 ዓ.ም የተወሰነ ማሻሻያ ቢታከልባቸውም)።
ነገር ግን ሕጎችን በማወጅ ብቻ ሳይሆን፤ በግል አርአያነትና ጥረትም አገሬውን ወደ ስልጣኔ ለማራመድ ሙከራዎች ተደርገዋል። “በለውጥ ላይ የምትገኝ ኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ በ1948 ዓ.ም ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀረቡ ሲሞን ሜሲን፤ በ1925 ገደማ ዓ.ም የንጉሡ ሴት ልጅ መሞቷን ጠቅሰው፤ ለሟቿ ልዕልት የተዝካር ድግስ እንደማይዘጋጅ በአዋጅ መነገሩን ይገልፃሉ። ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች ያለ አቅማቸው በሚደግሱት ተዝካር ኑሯቸው መናጋቱ ብቻ አይደለም ችግሩ። የየአካባቢው የመንግስት ባለስልጣናት በየፊናቸው ተዝካር ሲደግሱ፤ የአካባቢው ነዋሪና ገበሬ፤ ወደደም ጠላም፤ እህል፣ ከብት እና ገንዘብ እንዲያዋጣ ይገደዳል። ገበሬዎችን ከዚህ ልማዳዊ ሸክም ለመገላገል ነበር የንጉሡ ሙከራ – ይላሉ ፀሐፊው።
ይህም ብቻ አይደለም። የድሮ ለቅሶ እንደዛሬ አይደለም። በእርግጥ ዛሬም ቢሆን፤ የአገራችን ለቅሶ ለታይታ የሚቀርብ ቅጥ ያጣ ልማድ ነው። ግን የድሮው ይብሳል። ሰው ሲሞት፣ ልብስ መቅደድና ፀጉር መንጨት፤ ፊት መቧጨርና ደረት መደለቅ፤ መሬት ላይ መንከባለልና አፈር መልበስ የተለመደ ነበር። ነውጠኛ ለቅሶ ይሉሃል ይሄ ነው። ይህን ለማስቀረት ንጉሡ እንደጣሩ የሚገልፁት ሲሞን ሜሲን፤ ነጠላ አዘቅዝቆ መልበስ የተጀመረው ያኔ ነው ይላሉ። Changing Ethiopia፡ Simon D. MessingSource: Middle East Journal, Vol. 9, No. 4 (Autumn, 1955), pp. 413-432።
እንዲህ በየመስኩ የስልጣኔ ጭላንጭሎች ብቅ ብቅ ቢሉም፤ የ1960ዎቹ ተማሪዎችና ወጣት ምሁራን፤ በንጉሡ ደስተኛ አልነበሩም። እንዲያውም፤ ንጉሡን እንደ ዋነኛ ጠላት ፈርጀዋቸዋል። “ንጉሡ አገሪቱን በኋላቀርነት አስረው ይዘዋል። ህዝቡን ከትምህርት አራርቀውታል፤ በተለይ ሴቶች በመሃይምነት ጨለማ ተውጠዋል (ድርብ ጭቆና እንዲሉ)። ህዝቡ ከመሰረተ ልማትና ከኢኮኖሚ እድገት፣ ከኤሌክትሪክና ከስልክ፣ ከመንገድና ከትራንስፖርት አገልግሎቶች እንዳይተዋወቅ፤ የእርሻና የኢንዱስትሪ እድገት እንዳያይ ያደረጉት ንጉሡ ናቸው” የሚሉ ውግዘቶች፤ በያኔዎቹ “የአብዮታዊ ትውልድ” አባላት እንደተጀመሩ እስከዛሬ ዘልቀዋል።
እውነታው ግን፤ ሙሉ ለሙሉ የዚህ ተቃራኒ ነው። በእርግጥ፤ የንጉሡን ዘመን በብዙ ምክንያቶች መተቸት ይቻላል። “የአገሪቱ የስልጣኔ ጅምር ተንቀራፈፈ፤ መፍጠን ነበረበት” ብሎ መተቸት ስህተት አይሆንም። በአብዮቱ የመጣው ለውጥ ግን፤ ጭራሽ የስልጣኔ ጅምርን አዳፍኖ የሚደመስስ ሆነ። ከንጉሡ ድክመት ይልቅ “የአብዮታዊው ትውልድ” ጥፋት በብዙ እጥፍ ይልቃል። “የአብዮታዊው ትውልድ” በርካታ አባላት ታዲያ፣ ይህ ታሪካዊ ውድቀታቸውና ኪሳራቸው በግልፅ እንዲታወቅ አይፈልጉም። ለዚህም ነው፤ እንደያኔው አሁንም ጨምር፤ የንጉሡን አስተዳደር ከማውገዝና ከማጥላላት ያልቦዘኑት። ነገር ግን እውነታውን ለዘላለም መሸፈን አይችሉም። የንጉሡንና የአብዮቱን ዘመናት፤ የዛሬውንም ጭምር ለመመዘንና ለማነፃፀር የምንችልባቸው መረጃዎች ብዙ ናቸው። ዛሬ ጥቂቶቹን ብቻ እንመልከት።

ትምህርት ከጀማሪ እስከ ዩኒቨርስቲ
በ1938 ዓ.ም የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር፣ 35ሺ እንደነበር የሚገልፁት ዶ/ር ተከስተ ነጋሽ፣ ከአስር አመት በኋላ 95ሺ እንደደረሰ ይገልፃሉ – ዘጠኛ ሺ ገደማ የአንደኛ ደረጃ፣ አራት ሺ ገደማ የሁለተኛ ደረጃ፣ አራት መቶ ገደማ የከፍተኛ ትምህረት ተማሪዎች። በ1955 ዓ.ም፣ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች አስር ሺ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ደግሞ 305 ሺ መድረሱን ዶ/ር ተከስተ ጠቅሰዋል – በወቅቱ የስምንተኛ ክፍል ተማሪ እንደነበሩ በማስታወስ Education in Ethiopia Nordiska Afrikainstitutet, Uppsala። እንደገና ከአስር አመት በኋላ በአብዮቱ ዋዜማ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር 1.04 ሚሊዮን ደርሷል – በሃያ አመታት ውስጥ ከአስር እጥፍ በላይ በማደግ።
በደርግ ዘመን፣ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት የተመዘገበው የተማሪዎች ቁጥር ወደ 2.9 ሚሊዮን ገደማ ነው – በሶስት እጥፍ አድጓል ማለት ነው። በኢህአዴግ 20 አመታት ውስጥስ? የተማሪዎቹ ቁጥር ወደ 15 ሚሊዮን ገደማ ሆኗል። በደርግ ዘመን ከነበረው ቁጥር ጋር ሲነፃፀር በአምስት እጥፍ ይበልጣል።
በንጉሡ ዘመን በሃያ አመታት ውስጥ ከሃያ እጥፍ በላይ የጨመረው የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር በ1966 ዓ.ም 190ሺ ገደማ እንደደረሰ የሚገልፀው የአለም ባንክ መረጃ፣ በደርግ ዘመን ወደ 900ሺ እንደተጠጋ ይገልፃል። የደርግ ዘመን የተመዘገበው የአራት እጥፍ እድገት ከንጉሡ ዘመን ያነሰ ነው። በኢህአዴግ ጊዜም እንዲሁ። ኢህአዴግ ደግሞ በሃያ አመታት ውስጥ ወደ አምስት እጥፍ ገደማ በማሳደግ 4.5 ሚሊዮን አድርሶታል።
የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ቁጥር፣ በንጉሡ ዘመን በሃያ አመታት ውስጥ፣ ከአራት መቶ ገደማ ወደ 6500 አካባቢ ጨምሯል – በአስራ አምስት እጥፍ። በደርግ ዘመን ወደ ሶስት እጥፍ ገደማ አድጎ 18ሺ የደረሰ ሲሆን፣ በኢህአዴግ የሃያ አመታት ጊዜ፣ እንደ ንጉሡ ዘመን ከአስራ አምስት እጥፍ በማደግ ከ350ሺ በላይ ሆኗል።

ትምህርት በወንዶችና በሴቶች
የአብዮተኞቹ አንዱ መፈክር፣ የፆታ እኩልነት የሚል አልነበር? እስቲ የሴት ተማሪዎችን ድርሻ እንመልከት። አብዮተኞቹ የንጉሡን ዘመን ሲያወግዙ ስትሰሙ፤ በአብዮቱ ዋዜማ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት፣ የሴቶች ድርሻ ከዜሮ በታች የነበረ ነው የሚመስላችሁ። ነገር ግን፣ የትምህርት ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በ66 ዓ.ም. ከአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች መካከል 32 በመቶ ያህሉ ሴቶች ነበሩ። በደርግ ዘመን የሴቶች ድርሻ ወደ 40 በመቶ ገደማ ደረሰ፣ በኢህአዴግ ደግሞ ወደ 47 በመቶ።
በከፍተኛ ትምህርት፣ እዚህ ግባ የማይባል ድርሻ የነበራቸው ሴቶች፣ በ1952 ዓ.ም ወደ 3 በመቶ ድርሻ ካገኙ በኋላ፣ በሶስት እጥፍ አድጎ በአብዮቱ ዋዜማ ወደ አስር በመቶ ገደማ ድርሻ ለመያዝ የበቁ ሲሆን፣ በደርግ ዘመን የሴቶች ድርሻ ወደ 18 በመቶ አድጓል። በኢህአዴግ ዘመን ደግሞ፣ ወደ 30 በመቶ ገደማ ደርሷል።
በሴቶች ትምህርት ዙሪያ ፈጣን እድገት የተመዘገበው መቼ እንደነበር፤ ይሄው መረጃው ራሱ ይናገራል።
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ላይም አብዮተኞቹ ለውጥ አላመጡም። በንጉሡ ዘመን፣ በመጨረሻዎቹ ሃያ አመታት፣ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ከሰላሳ እጥፍ በላይ ስለጨመረ፣ የተማሪዎቹ ቁጥር በአብዮቱ ዋዜማ 8700 ገደማ ደርሶ ነበር። በደርግ ዘመን የታየው እድገት ኢምንት ነው። የተማሪዎች ቁጥር ከአስር ሺ ብዙም ፈቀቅ አላለም። በመጀመሪያዎቹ የኢህአዴግ አስር አመታትም እንዲሁ፣ የእድገት ፍንጭ አልታየም። ከዚያ በኋላ ነው በፍጥነት ማደግ የጀመረው። በኢህአዴግ ሃያኛ አመት ላይ፣ የቴክኒክና ሙያ ተማሪዎች ቁጥር፣ ከሰላሳ እጥፍ በላይ በማደግ ከ350ሺ በላይ ሆኗል።

የ“መሰረተ ልማት” አቅርቦት
በ1947 ዓ.ም፣ በአገሪቱ የነበረው አመታዊ የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት፣ 33 ጊጋዋትሃወር እንደነበር የውሃ ሚኒስቴር ባለሙያ መረጃ ያሳያል። በአማካይ ለአንድ ሰው 1600 ዋትአወር… በጣም ትንሽ ነው። ለአንድ ቤተሰብ በቀን ለ25 ደቂቃ አንድ አምፖል ብቻ ያበራ ነበር እንደማለት ነው። እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ ሃያ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግን፣ አቅርቦቱ በ18 እጥፍ ጨምሯል። 18 እጥፍ? ፈጣን እድገት ነው።
የአለም ባንክ መረጃ እንደሚያሳየው፣ በአብዮቱ ዋዜማ አመታዊው የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት 590 ጊጋዋትአወር ደርሶ ነበር። ግን በእነዚሁ አመታት ውስጥ የሕዝብ ቁጥርም ስለጨመረ፣ የኤሌክትሪክ ሃይል የማግኘት እድል በ18 እጥፍ ሳይሆን በ11 እጥፍ ነው የጨመረው። ይሄም ቀላል አይደለም። በቤተሰብ በየቀኑ 5 ሰዓት ያህል አምፖል እንደማብራት ቁጠሩት። ይሄ በንጉሡ ዘመን ነው።
በደርግ ዘመንስ? በ17 የደርግ አመታት ውስጥ፣ የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት 1210 ጊጋዋትአወር ነው የደረሰው። በንጉሡ ዘመን ከነበረው ጋር ሲነፃፀር በአንድ እጥፍ ብቻ ነው የጨመረው። ግን ኢትዮጵያውያን የኤሌክትሪክ ሃይል የማግኘት እድላቸው ብዙም አልጨመረም። ለምን ቢባል፣ የሕዝብ ቁጥርም ጨምሯላ። እናም፣ በቤተሰብ ሲሰላ፣ በየቀኑ 6 ሰዓት ለማይሞላ ጊዜ አንድ አምፖል የማብራት ያህል ነው። በአጭሩ፣ በደርግ ዘመን ኤሌክትሪክ የመጠቀም እድል የተሻሻለው፣ ከሰባት በመቶ ባነሰ መጠን ነው።
በኢህአዴግ ዘመንስ? ከ1983 ዓ.ም እስከ 2003 ዓ.ም ድረስ ያለውን የሃያ አመታት እድገት እንመልከት። የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦቱ በምን ያህል ጨመረ? አሁንም የአለም ባንክ መረጃን ነው የምጠቅሰው። በጊጋዋትአወር፣ 1210 የነበረው ወደ 5000 ገደማ ጨምሯል። በአራት እጥፍ ገደማ ማለት ነው። ነገር ግን፣ በንጉሡ ዘመን እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ በነበሩ ሃያ ዓመታት፣ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ከ18 እጥፍ በላይ ማደጉን መዘንጋት የለብንም። በደርግ ዘመን ከነበረው ጋር ሲነፃፀር ግን፣ በኢህአዴግ ዘመን የታየው እድገት በእጅጉ የተሻለ ነው። ሰዎች በኤሌክትሪክ የመጠቀም እድላቸውስ ምን ያህል ተሻሻለ? በኢህአዴግ ሃያ አመታት ውስጥ፣ ከአንድ እጥፍ በላይ ተሻሽሏል። በቤተሰብ ሲሰላ፣ በየቀኑ ወደ 15 ሰዓታት ያህል አንድ አምፖል ለማብራት የሚችል የኤሌክትሪክ ሃይል ተገኝቷል እንደማለት ነው።
እንግዲህ አስቡት። በ1947 ዓ.ም አንድ የኢትዮጵያ ቤተሰብ በአማካይ በየቀኑ ለ25 ደቂቃ ብቻ አንዲት አምፑል ማብራት ይችል ነበር። በ1966 ዓ.ም፣ በየቀኑ ለ5 ሰዓታት ያህል ማብራት ቻለ። በ1983 ዓ.ም ወደ 6 ሰዓት ያህል ፎቀቅ አለ። በ2003 ዓ.ም፣ ወደ 15 ሰዓት ገደማ አደገ። የትኛው ዘመን እድገት ይሻላል?
እንደ ኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት ሁሉ፤ የመንገድ ግንባታ፣ የአውሮፕላን ትራንስፖርትና የስልክ መስመር አገልግሎትም እንዲሁ፤ ከአብዮቱ ዘመናት ይልቅ በንጉሡ ጊዜ የተሻለ እድገት ተመዝግቧል። ለምሳሌ በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ፤ ከ1950 ዓ.ም እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ ወደ ስድስት እጥፍ ገደማ በመስፋፋት፣ 45ሺ ገደማ የስልክ መስመሮች አገልግሎት ላይ ውለዋል።
በደርግ ዘመንስ? በሁለት እጥፍ ገደማ ነው ያደገው – ወደ 135ሺ ገደማ የስልክ መስመሮች። እንደ ንጉሡ ዘመን ከስድስት እጥፍ በላይ እድገት የታየው በኢህአዴግ ዘመን ነው። የስልክ መስመሮች ቁጥር በሃያ አመታት ውስጥ 900ሺ ደርሰዋል።
ይህም ብቻ አይደለም። እስከ አብዮቱ ዋዜማ ድረስ፣ የኤክስፖርት ገበያ አራት እጥፍ ገደማ አድጓል – ከ70 ሚሊዮን ዶላር ወደ 270 ሚሊዮን ዶላር። በደርግ ዘመን፣ በእነዚያ ሁሉ አመታት፣ የኤክስፖርት ገበያ በአንድ እጥፍ እንኳ ማደግ አልቻለም። ከ470 ሚሊዮን ዶላር አካባቢ አላለፈም። በኢህአዴግ ዘመንም በመጀመሪያዎቹ አስር አመታት፣ ከኤስፖርት ገበያ የተገኘው ገቢ እዚያው ገደማ ተገድቦ ቆይቷል። ከዚያ በኋላ ነው ከቀድሞው የተሻለ ፈጣን እድገት መታየት የጀመረው። በጥቅሉ፣ በሃያ የኢህአዴግ አመታት ውስጥ እስከ 2003 ዓ.ም ድረስ የኤክስፖርት ገቢ፣ ከአራት እጥፍ በላይ በማደግ፣ ከ2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሆኗል – በንጉሡ ዘመን ከተመዘገበው እድገት ጋር ተቀራራቢ ነው።

የእህል ምርትና እጦት
የእህል ምርትን ደግሞ እንመልከት። ከአብዮቱ በፊት በነበሩ 20 ዓመታት፣ ለአንድ ሰው በአማካይ በየአመቱ 175 ኪሎ ገደማ እህል ይመረት ነበር። በአብዮቱ ዘመናት በደርግ ጊዜስ? ለአንድ ሰው በአማካይ 135 ኪሎ ገደማ እህል ነው በየዓመቱ ሲመረት የነበረው። በሌላ አነጋገር፤ የሕዝብ ብዛትን ከግምት አስገብተን ስናሰላው የእህል ምርት፣ በንጉሡ ዘመን የ30 በመቶ ብልጫ ነበረው።
በኢህአዴግ ዘመንስ? በመጀመሪያዎቹ የኢህአዴግ አስር አመታት፣ የአገሪቱ የእህል ምርት፣ ከደርግ ዘመንም የባሰ ነበር – በየአመቱ በአማካይ ለአንድ ሰው 125 ኪሎ እህል ነበር የሚመረተው። ቀጥለው ባሉት አስር አመታትስ? ምርቱ በአማካይ ወደ 165 ኪሎ ግራም ገደማ ደርሷል። በእርግጥ ያለፉትን ስምንት አመታት ብቻ ካየን፣ የአገሪቱ የእህል ምርት እየተሻሻለ፣ በአማካይ 175 ኪሎ ገደማ እንደደረሰ እናያለን። በአጠቃላይ ሲታይ፤ ከአብዮቱ ዋዜማ ጀምሮ ወደ ታች ሲያሽቆለቁል የነበረው አብዮታዊ የውድቀት ጉዞ ቀስ በቀስ የተገታው፤ የሶሻሊዝም አብዮት ከተገታ በኋላ ነው። ቀስ በቀስም እያገገመ፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ በንጉሱ ዘመን ወደ ነበረበት ደረጃ ለማደግ ችሏል። በሌላ አነጋገር፤ ኢትዮጵና ኢትዮጵያዊያን በአብዮቱ ሳቢያ ለድህነትና ለረሃብ ከመዳረጋቸው በተጨማሪ፤ ለ30 አመታት ያህል የኋሊት ተጉዘዋል። አዲሳድማስ ጋዘጣ ነጻ አስተያየት

ብሄር ብሄረሰብ፤ የዘር ፓለቲካ… ደስታው አንዳርጌ (ዶ/ር)

እውቀት ይስፋ፣ ድንቁርና ይጥfa
ይህ ነው የኢትዮጵያ ተስፋ።
ተስፋ ገብረሥላሴ
ፊደል የቆጠርሁት በአገራችን የህትመት ፋናወጊ (እና አርበኛ) የሆኑት ተስፋ ገብረሥላሴ ያሳትሟት በነበረው የባለ ፲ ሣንቲም ፊደል ነበር። ከፊደሏ ሽፋን ላይ ታዲያ ‘ተስፋገብረሥላሴ ዘብሄረ ቡልጋ’ ይላል። መጠየቅ እወድ ነበርና መርጌታን ‘የንታ ብሄረ ቡልጋ ምን ማለት ነው?’ ብየ ጠየኳቸው። የንታም ልጄ ብሄር ማለት በግእዝ አገር ማለት ነው። ቡልጋ ደሞ ሽዋ ክፍላገር ውስጥ የሚገኝ አውራጃ ነው። የተስፋ ገብረሥላሴ አገር እዚያ ነው፤ አሉኝ።
ከዚያ አስኮላ ትምርት ገብቸ ፬ኛ ክፍል ህብረተሰብ መጽሀፍ ውስጥ የኢትዮጵያ ‘ብሄረሰቦችን’ የሚያሳይ ስዕል ተደርድሮ አየሁ። በተለይ ሲዳማን የዎከሉት ቆንጃጅት ሙገጫ ሲዎግጡ የሚያሳየው ስእል አይረሳኝም። ይሁን እንጅ ብሄረሰብ የሚለው ቃል አልገባኝም ነበርና አስተማሪየን ጠየኳት። እሷ ግን ጎሳ፣ ነገድ ቅብጥርሴ ብላ የባሰ ግራ አጋባችኝ። ደግነቱ ማታ ማታ የንታ ዘንድ ወንጌል እማር ነበርና ወንበር ከመጀመሩ በፊት ቀደም ብዬ ሄጄ የንታን ‘ብሄረሰብ ምን ማለት ነው?’ ብዬ ጠየኳችው። የንታም ብሄር ማለት አገር ነው፣ ሰብ ደሞ ሰው ማለት ነው። እንግዲህ ብሄረሰብ ያው የሰው አገር መሆኑ ነዋ አሉኝ። የበለጠ ግራ ተጋባሁ። ህብረተሰብ መጽሀፌ ውስጥ ያዬሁት የሚያማምሩ ቆንጃጅትን ምስል እንጅ ወንዝ ወይ ጋራና ሸንተረር አልነበረማ።Ethiopia and Eritrea map
ሁሉ ሆነና ደርግም በኢሕአዴግ ተተካ። አሁን ግራ ያጋባኝ የነበረው ‘ብሄረሰብ’ የሚለው ቃል ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ ተብሎ ተራብቶ መጣ። የግዕዙን ቀጥተኛ ትርጉም ካየን እንግዲህ አገራት፣ የሰው አገራትና ህዝቦች እያልን መሆኑ ነው። ይሁንና ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች ተብለው ይጠሩ የነበሩት የሁሉም ቋንቋ ተናጋሪዎች አሁን ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ ሆነው የተባዙት አንዳንዶቹ ብሄረሰቦች ወደ ብሄርነት ሌሎቹ ደግሞ ወደ ህዝብነት ተለውጠው ይሁን በሌላ ምክንያት በውል አይታዎቅም። በአንጻሩ አሁን የኢትዮጵያ ህዝብ ብሎ ነገር የለም። በኢትዮጵያ ሕገ፡መንግስት ውስጥ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚል ቃል አይገኝም። ፖለቲከኞችም ‘የኢትዮጵያ ህዝቦች’ እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብ ሲሉ አትሰሙም። ይህ አጋጣሚ የሚመስለው ካለ እሱ የዋህ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ማለት (ልክ በኢህአዴግ የመጀመሪያዎቹ ሰባት የስልጣን አመታት ኢትዮጵያ አገሬ የሚል ዘፈን እንደማዳመጥ ያለ) በትምክህተኝነት ሊያስከስስ የሚችል የፖለቲካ ፋውል መሆኑን እያንዳንዱ ካድሬ ስለሚረዳ ነው።
የኢትዮጵያ ሕገ፡መንግስት በአገሪቱ ውስጥ የፖለቲካ ስልጣኑም ሆነ ምድሩ አንዲሁም በላዩና በውስጡ ያለው ሀብት ሁሉ ‘የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ የጋራ ሀብት ነው ይላል። ይህ ደግሞ ከሌሎች ኣገሮች ሕገ፡መንግስታት ሁሉ ልዩ ያደርገዋል (ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የሚለው ሀረግ እንደ ዋሊያ ኢትዮጵያ ብቻ ነው የሚታወቀው)። ይህ ይገርመኝ ነበርና ከአስር ኣመታት በፊት ከህገ፡መንግስት ጋር በተገናኘ የመመረቂያ ጽሁፍ ሳዘጋጅ ለመሆኑ አነዚህ የኣገሪቱን የፖለቲካ ስልጣንና ሀብት ኣንድም ሳያስቀሩ ጠቅልለው የያዙ ፍጡራን በትክክል አነማን ናቸው? ኣንዳቸው ከሌላቸው የሚለዩት በምን ነው? በአገሪቱ ውስጥስ ስንት ብሄሮች፣ ስንት ብሄረሰቦችና ስንት ህዝቦች አሉ? ለምሳሌ የቀበሌ መታወቂያ ስትወስድ ብሄርህን ተጠይቀህ ጉራጌ ብለህ ከሞላህ በኋላ ማታ በኢቲቪ የጉራጌ ብሄረሰብ ስላስመዘገበው ልማት ትሰማለህ። ታዲያ ብሄርና ብሄረሰብ አንድም ሁለትም ናቸው? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎችን ይዠ መልስ ፍለጋ ሰነዶች ማገላበጥ ነበረብኝ። የህገ፡መንግስቱን ረቂቅ (ፕሪፓራቶሪ ዎርክስ) ሳይቀር አገላብጨ የሚረባ ነገር ላገኝ አልቻልሁም። ሕገ፡መንግስቱን በማርቀቅ የጎላ ድርሻ ነበራቸው የሚባሉትን ሰዎችም ጠይቄ ያገኘሁት ውጤት ኣልነበረም። በጣም ተገረምሁ። በአገራችን ላይ ከፈጣሪ ቀጥሎ ሁሉን ሀብትና ስልጣን ‘የተቆጣጠሩት’ ግኡዛን ማንነት እንዴት አይታዎቅም? ይህ እኮ እጅግ መሰረታዊ ጥያቄ ነው።
በተለይ ህዝቦች የሚለው ቃል ግራ አጋቢ ነው። በአለም ላይ አንድ ቋንቋ ተናጋሪ ወይም እንድ አይነት ማንነት ያላቸው ሰዎች ብቻ የሚኖሩባቸው አገራት ከአምስት አይበልጡም፤ ይህም ቢሆን በጣም የሚያከራክር ነው። ይሁን እንጅ የብራዚል ህዝቦች ወይንም የኬንያ ህዝቦች ቢባል እንግዳ ነው የሚሆነው። ምክንያቱም ህዝብ በትርጉሙ ያልተወሰነ ቁጥርና ማንነት ያላቸው ሰዎችን ያካተተ የጥቅል (የወል) ስም ስለሆነ ነው። ለዚህም ነው የአለም ህዝብ ቁጥር እንጅ የአለም ህዝቦች ቁጥር የማንለው። በርግጥ ፈረንጆቹም ከቅኝ በፊት ይኖሩ የነበሩ ቀደምት ጎሳዎችን (ትራይብስ) ለማመልከት ኢንዲጅነስ ህዝቦች ወይም አማዞን ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦች ይላሉ። ይህ ግን ቀደምት ጎሳዎችን (ነገዶችን)የሚተካ ተለዋጭ ቃል እንጂ ተደራቢ ስያሜ አይደለም። ስለሆነም ቀደምት ጎሳዎችና ኢንዲጅነስ ህዝቦች አይሉም። እንዲያውም ኢንዲጅነስ ህዝቦች የየአገራቸው (ሰፊ)ህዝብ አካል ናቸው። ለምሳሌ የካናዳ ህዝብ በአገሩ የሚኖሩ ኢንዲጅነስ ህዝቦችን ያጠቃልላል። በዚህ አግባብ ከመደበኛ ሰዋሰው ርባታ ተቃራኒ ቢመስልም በአንድ አገር ውስጥ ህዝብ የሚለው ቃል ህዝቦች ከሚለው ቃል ይሰፋል ማለት ነው። ከላይ በጠቀሁት ምሳሌ የካናዳ ህዝብ ካናዳዊያንን በሙሉ ሲያመለክት የካናዳ ኢንዲጅነስ ህዝቦች ግን የካናዳ ህዝብ አካል የሆኑ (ከአጠቃላዩ ህዝብ ፭ ፕርሰንት እንኳን የማይሞሉ) ግን ደግሞ የየራሳቸው የተለየ ማንነት ያላቸውን ነገዶችን ብቻ የሚያመለክት ነው። በሁሉም አገሮች የሚኖሩ የተለያዬ ቋንቋና ማንነት ያላቸው ሁሉ በአንድ ላይ የዚያ አገር ህዝብ ተብለው ነው የሚታዎቁት።
ወደ አገራችን ስንመጣ ግን ሁለት አደናጋሪ ነገሮችን እናገኛለን። የመጀመሪያው ህዝቦች የሚለው ቃል አግባብ በሌላው አለም እንደሚታወቀው ሁሉ ቀደምት ነዋሪወችን (ኢንዲጅነስ ትራይብስ) ለማመልከት ነው እንዳይባል ኢትዮጵያ ውስጥ ቀደምት ያልሆነው ማን እንደሆነና ማን ከማን እንደሚቀድም አይታወቅም። እንዲያውም ሁሉም ‘ብሄር ብሄረሰቦች’ ቀደምት ነዋሪወች ናቸው ማለት ይቻላል። ቢያንስ ይህ ላለመሆኑ ተቃራኒ ማስርጃ የለም (እንዲያውም እኮ እንደ ሳይንሱ ከሆነ የአለም ህዝብ ሁሉ የተገኘው ከኢትዮጵያ ነው)። ‘ህዝቦች’ የሚለው ቃል አንዳንዶች እንደሚሉት አናሳ ቁጥርና አገራዊ የፖለቲካ ተሳትፎ ያላቸውን የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪዎችን ለማመልከት ነው እንዳንል እነሱው መልሰው ታዳጊ ብሄረሰቦች (አንዳንዴ አናሳ ብሄረሰቦች) ሲሏቸው እንሰማለን። ያ ከሆነ ደግሞ ብሄር ብሄረሰቦች በሚለው አገላለጽ ብንስማማ እንኳን ‘ህዝቦች’ የሚለው ቃል አላስፈላጊ ድግግሞሽ ከመሆንና ከማደናገር ኣልፎ የሚጨምረው ነገር የለም ማለት ነው። ሁለተኛውና በጣም የሚገርመው በአለም ላይ ባልተለመደ ሁኔታ በአገሪቱ የሚኖሩት ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ በአንድላይ የኢትዮጵያ ህዝብ አይሆኑም። ይህ የሆነው አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት ሕገ፡ መንግስታዊ ቃልኪዳን ገብተናል ያሉት ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ የሚጋሩት ማንነት ሳይኖራቸው ቀርቶ ይሁን በሌላ ምክንያት አይታወቅም። ለነገሩ የአንድ አገር ህዝብ አካል ለመሆን የዚያ አገር ዜጋ ከመሆን ሌላ ምን የተለየ የጋራ ማንነት ያስፈልጋል?
ግድየለም፤ ያ ሁሉ ፖለቲካ ነው ብለን እንለፈው። እኛስ ቢሆን ቃላትን (አንደኣብዛኛዉ ነገራችን) እንደልባችን የምንጠቀመው ለምን ይሆን? ኢትዮጵያ በዘር ተከፋፈለች፣ የዘር ፖለቲካ ያጠፋናል፣ የጦር ሰራዊቱ ከኣንድ ዘር በወጡ አዛዦች ቁጥጥር ስር ነው፣ አቶ እከሌ በተቋሙ ውስጥ የነገሰውን ዘረኝነት በመቃዎም ስልጣናቸውን ለቀቁ፣ ወዘተ…በየቀኑ የምንሰማው ሮሮ ነው። ለመሆኑ ዘር ምንድን ነው? ኢትዮጵያ ውስጥ ስንት ዘር አለ? ለምሳሌ አማራ አንድ ዘር ትግሬ ደግሞ ሌላ ዘር ናቸው? ከሆነስ ከየት ነው የመጡት? እንደሚታወቀው ያን ያህል ሩቅ ከማይባል ጊዜ በፊት ግእዝ እንጂ ትግርኛም አማርኛም ኣልነበሩም። ታዲያ ያኔ ትግሬ ነበር? ኣማራስ? ሌላው ቀርቶ ሴሜቲክ፣ ኩሽቲክ የሚባለውስ ምናልባት ቋንቋን ከመግለጽ (ይህም አከራካሪ ይመስለኛል) የዘለለ ያለው አንድምታ ምንድን ነው? ለነዚህ ጥያቄዎች መልስ መስጠት ችሎታየም አላማየም አይደለም፤ ነገር ግን በጥንቃቄ መታየት የሚገባቸው መሰረታዊ ጥያቄዎች ይመስሉኛል። እንዲያውም ስለማንነታችን ሳይንሳዊ ብንሆን ብዙ ችግራችን የሚቃለል ይመስለኛል። ኢሕአዴግ ኢትዮጵያ ውስጥ ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ እንጅ እናንተ ቦታ የላችሁም፤ መሬቱ በሙሉ የእነሱ በመሆኑ እናንተ የመሬት ባለቤት መሆን አትችሉም ሲለን ቢያንስ እነዚያ ‘ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች’ በትክክል እነማን እንደሆኑ እንዲነግረን እንጠይቃለን። በአንጻሩ ደግሞ እኛ የዘር ፖለቲካ ወዘተ…ስንል ምን ማለታችን እንደሆነ መረዳትና ማስረዳት ያለብን ይመስለኛል።
[email protected]
በዚሁ ላብቃ።
ሰላም

ባለፉት አራትና አምስት አመታት በግልጽ እንዳየነዉ የኢትዮጵያ ህዝብ እኩልነቱን፤ መብቱንና ነጻነቱን ለማስከበር የሚያደርገዉ ትግል ጫና በፈጠረበት ቁጥር ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ የራሱን ህገመንግስት የሚደፈጥጡ ህጎች አርቅቆ አያጸደቀ ሠላማዊ ዜጎችን አስሯል፤ ገድሏል ከአገር እንዲሰደዱም አድርጓል። ለምሳሌ በ2003 ዓም የኢትዮጵያ ፓርላማ ከቤተመንግሰት የተላለፈለትን ትዕዛዝ አክብሮ ለኢትዮጵያ ህዝብ መብትና ነፃነት መከበር የሚታገለዉን የግንቦት 7 ንቅናቄ ሽብርተኛ አድርጎ ፈርጇል። ይህ ፈር የለቀቀ ፍረጃ ደግሞ ወያኔ የሱን ዘረኛ ስርዐት የሚቃወሙ ግለሰቦችን፤ ሀሳባቸዉን በነፃነት የሚገልጹ ዜጎችን፤ ጋዜጠኞችን፤ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችንና ከወያኔ ጋር አናብርም ያሉ ወጣት ኢትዮጵያዉያንን “ግንቦት ሰባቶች” ናችሁ እያለ በጅምላ እያሰረ እንዲያሰቃይ ህጋዊ ሽፋን ሰጥቶታል። ለምሳሌ ከፍትህና ከነጻነት ጥማት ዉጭ ከግንቦት 7 ንቅናቄ ጋር ምንም አይነት ግኑኝነት የሌለዉን የፖለቲካ ፓርቲ መሪዉን አንዱአለም አራጌን፤ ታዋቂዉን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋንና መምህርት ርኢዮት አለሙን የግንቦት 7 አባላት ናቸዉ የሚል ሰንካላና መሠረተ ቢስ ክስ መስርቶ ለረጂም ዘመን እስራት ዳርጓቸዋል።
ወያኔ እንደ ዛሬዉ ከተማ ዉስጥ ሆኖ ሥልጣን ሳይቆጣጠር ገና ጫካ ዉስጥ እያለ ጥርሱን ከነከሰባቸዉና ከተቻለ አጠፋቸዋለሁ ካለዚያም አሽመደምዳቸዋለሁ ብሎ አስራ ሰባት አመት ሙሉ ከተዘጋጀላቸዉ የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ የአማራ ብሄረሰብ ነዉ። በለስ ቀንቶት ሥልጣን ከጨበጠ ማግስት ጀምሮም በወሎና በጎንደር በኩል ከትግራይ ጋር የሚያዋሰኑ ሰፊ የሆነ ለም መሬቱን ጠቅልሎ በመውሰድ ዘረኛ ሥርዓቱን ዕድሜ ሊያራዝሙልኛል ይችላሉ ብሎ የሚተማመንባቸውን የቀድሞ የትግል አጋሮቹንና ካድሬዎቹን አስፍሮበታል:: ይህ በደልና ግፍ አልበቃ ብሎትም ቀደምቶቹ የኢትዮጵያ ገዥዎች ለፈጸሙት ግፍና የአስተዳደር በደሎች ሁሉ አማራዉን በጅምላ ተጠያቂ የሚያደርግ ፕሮፖጋንዳ እነሆ እስከዛሬ በመርጨት ለዘመናት በሠላም ከኖረው ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር በጠላትነት እንዲተያይ አድርጎታል:: በወያኔ አጋፋሪነት በበደኖ ፡በአርሲ በአረካና ሌሎች አካባቢዎች አማራው ላይ በግፍ የተፈጸመው ጭፍጨፋና ከ2004 እስከ 2005 ዓም አማራዉን ከጉራፈርዳና ከቤንሻንጉል ለማፈናቀል የተወሰደው እርምጃ የዚህ የወያኔ የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ ውጤት መሆኑን የምስት የለም::
ሟቹ መለስ ዜናዊና በህይወት የሚገኙ ቀንደኛ የወያኔ መሪዎች የተጠናወታቸው የአማራ ጥላቻ በጸረ ፋሽስት ዘመቻ ወቅት ባንዳ ከነበሩ አባቶቻቸዉና አያቶቻቸዉ የተወረሰ ፋሽስት ጣሊያን ለደረሰባት ሽንፈት በዘርና በሃይማኖት ተከፋፍለን እርስ በርሳችን እንድንጠፋፋ ተክላብን የሄደቺው ተንኮል አካል ነው ::
የዚህ የጥፋት አጀንዳ አስፈጻሚ የሆነው ወያኔ የጀመረውን አገር የማፍረስና ህዝብ የመከፋፈል አጀንዳ ለማሳካት በየክልሉ የተኮለኮሉ ምስሌኔዎች እንወክለዋለን በሚሉት ህዝብና ክልል ላይ እየፈጸሙት ያለው በደልና ሰቆቃ አዲስ ምዕራፍ በያዘበት በአሁኑ ወቅት እራሳቸዏን ለባርነት አዋርደው ህዝባቸውን በማዋረድ ላይ የሚገኙት የብአዴኑ አለምነህ መኮንንን የመሳሰሉ ሆድ አደሮች ውርደት በቃን ዘረኝነት በቃን ብለው በተነሱ ዜጎች ላይ እየወሰዱ ያለው ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ እጅግ አሳሳቢ ሆኖአል::
ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና ሞክራሲ ንቅናቄ ከሰሞኑ በደረሰው መረጃ ወያኔ ከአማራው ቀምቶ በትግራይ ክልል ባስገባቸው ወረዳዎች ላይ የሚኖሩ ንጽሃን ዜጎች ለምን በወያኔ የግፍ አገዛዝ ትማረራላችሁ እየተባሉ በወያኔ ታማኝ ሚሊሻዎች
እስር እንግልትና ድብደባ እየተፈጸመባቸው መሆኑን አረጋግጦአል:: በዚህ በአዲስ መልክ በተጀመረዉ የወያኔ የጥቃት ዘመቻ መሳሪያ ያነገቡ የህወሃት ሚሊሻዎች ከክልላቸዉ ዉጭ ወደ ተለያዩ የአማራ ከተማዎችና ወረዳዎች ሰርገዉ እየገቡ የእነሱን ቋንቋ የማይናገረዉን ሁሉ የግንቦት 7 ተላላኪዎች ናችሁ በሚል እያሰሩ በመደብደብ ላይ ናቸዉ።
ይህ በመሆኑ ዛሬ አትዮጵያን ከሱዳንና ትግራይን ከጎንደር ጋር በሚያዋስኑ የአማራ ክልል ዉስጥ የሚገኙ ገበሬዎች እጃቸዉ እርፍ ከሚጨብጥበት ግዜ በወያኔ ሰንሰለት የሚታሽበት ግዜ ይበልጣል፤ የመንግስት ሰራተኛዉና የከተማ ነዋሪዉም ቢሆን አብዛኛዉን ግዜ የሚያጠፋዉ ከወያኔ ካድሬዎች ጋር ግምገማ በመቀመጥ ሲሆን ተማሪዉና ወጣቱ ህብረተሰብ ደግሞ “መጡ አልመጡም” እያለ ሌሊቱን የሚያሳልፈዉ በየጫካዉ እየተሸሸገ ነዉ።
የዚህ አይነት አስከፊ ግፍና መከራ በአፋር ፡ በጋምቤላ በኦጋዴንና በኦሮሚያ በሚኖሩ ዜጎቻችን ላይ ሲፈጸም ቆይቶአል:: ? ወያኔ እራሱ አርቅቆ ባጸደቀውና በሐምሌ ወር 1987 ዓም በስራ ላይ የዋለዉ የወያኔ ህገ መንግስት ኢትዮጵያ በዘጠኝ የፌዴራል ክልሎች መከፈሏንና እያንዳንዱ ክልል እራሱን በእራሱ የማስተዳደር መብቱ የተረጋገጠ እንደሆነ ይደነግጋል። በዚህ ህገ መንግስት መሠረት እያንዳንዱ ክልል የራሱ ቋንቋ፤ የአስተዳደር ማዕከልና እንዲሁም የክልሉን ሠላምና ጸጥታ የሚያስከብር የፖሊስ ኃይል ይኖረዋል ይላል። ታድያ ለምንድነዉ እያንዳንዱ ክልል የራሱ ፖሊስ ኃይል አያለዉ ከትግርኛ ቋንቋ ዉጭ ሌላ ቋንቋ የማይናገሩ የህወሃት ታማኝ ሚሊሻዎች አማራ ክልል ዉስጥ እየገቡ አማራዉን የሚያሰቃዩት?
መልሱ ቀላል ነዉ። ኢትዮጵያ ዉስጥ ህዝባዊ አምቢተኝነቱ እያየለ በመጣና የነጻነት ኃይሎች ጡንቻ በፈረጠመ ቁጥር ወያኔ አንገቷ ላይ ቀጭል እንደታሰረባት በቅሎ ይደነብራል። የደነበረ ደግሞ መራገጡ አይቀርምና መሳሪያ ያነገቡ ኃይሎችን እንቅስቃሴ እገታለሁ በሚል ከንቱ ጥረት ደንባራዉ ወያኔ የፈሪ በትሩን በድንበር አካባቢ በሚኖሩ የአማራ ክልል አርሶ አደሮች፤ ወጣቶችና ሠራተኞች ላይ ማሳረፍ ጀምሯል።
ወያኔ እንደ ግንቦት ሰባት የኮነነዉና የህዝብና የአገር ጠላት አድርጎ የሳለዉ ድርጅት የለም፤ የወያኔ የዜና ማሰራጫዎችም ይህንን የአገዛዙን አቋም በተደጋጋሚ ለኢትዮጵያ ህዝብ አሰምተዋል።የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ማን ለመብቱና ለነጻነቱ እንደቆመና ማን መብቱና ነጻነቱ ላይ እንደቆመበት ለይቶ የሚያዉቅ ህዝብ ነዉ። ስለዚህም ግንቦት ሰባት ወያኔዎች አላፊዉንና አግዳሚዉን “ግንቦት ሰባት” ነህ እያሉ ከሚያሰቃዩ፤ ህዝብንና ግንቦት ሰባትን ያስተሳሰረዉ ነጻነት፤ ፍትህና ዲሞክራሲ ነዉና የኢትዮጵያን ህዝብ ጥያቄ ቢመልሱ ለእነሱም፤ ለእኛም ለአገርም ይበጃል የሚል የጸና እምነት አለዉ። ወያኔ በኢህአዴግ ስም ያሰጠጋቸዉን ምሰለኔዎች ጨምሮ ከራሱ ዉጭ ሌላ ማንንም አያምንም፤ ስለዚህም ነዉ የአገሪቱን የመከላከያ፤ የደህንነትና የፖሊስ ተቋሞች በራሱ ሰዎች ቁጥጥር ስር ያደረገዉ። ዛሬ በግልጽ እንደምንመለከተዉ ወያኔ በጉልበት ለያዘዉ ስልጣን ያሰገኛል ብሎ በሚጠረጥረዉ ቦታ ሁሉ የራሱን ልዩ ሚሊሺያ እየለላከ የኢትዮጵያን ህዝብ መኖሪያ ቤቱ ድረስ አየሄደ እያጠቃ ነዉ። ግንቦት ሰባት ወያኔና የፈጠረዉ ዘረኛ ስርዐቱ የቆሙት በፍጹም ማንሰራራት የማይችሉበትት የመጨረሻ መቀበሪያ ጉድጓዳቸዉ ጫፍ ላይ ነዉ የሚል ጽኑ እምነት አለዉ። ሆኖም ጉድጓድ ጫፍ ላይ የቆመ ጠላት በራሱ ተወርዉሮ ጉድጓዱ ዉስጥ አይገባምና ይህንን የተዳከመ ጠላት እተፈራገጠ ጉዳት ከማብዛቱ በፊት ለመደምሰስ ክንዳችንን አጠናክረን በህብረት እንደ አንድ ሰዉ እንነሳ ይላል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

እየደጋገምን የምናጠፋው ጥፋት እኛን ራሳችንን ይዞ እንዳይጠፋ መጠንቀቅ ያባት ነው!

ያለ ለውጥ፣ ያለ ዋስትና መራመድ አይቻልም፡፡
በማንኛውም ረገድ ራስን መቻል እንደሚኖርብን ልብ እንበል፡፡ በምግብ ራሳችንን ችለን ረሀብተኛ ዲሞክራሲ ይዘን እንጓዝ ብንል የማያዋጣንን ያህል፤ በባዶ ሆድም ዲሞክራሲን አንግቦ መጓዝ ወንዝ አያሻግረንም፡፡ ጥቂት የናጠጡ ሀብታሞችና አያሌ የኔ-ብጤዎች ያሏት ሀገርም ሆነ ሰላሟን አጥታ ብዙ ሀብታሞችን ያፈራች ሀገር እንድትኖረን አይደለም ደፋ-ቀና የምንለው፡፡

እንደጥንቱ መፈክር “ጉዟችን ረጅም ትግላችን መራራ” ነው ማለትም አያዛልቀንም፡፡ ሁሌም ረጅም፣ ሁሌም መራራ መሆን የለበትምና! ያለ ለውጥ፣ ያለ ዋስትና መራመድ አይቻልም፡፡ የለውጥ አንቀሳቃሹ በአብዛኛው ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ በዕውቀት የተገነባ፣ ለውጥ የገባው፣ ዛሬ ላይ የተደረሰው ብዙ ለውጥና መስዋዕትነት ታይቶ መሆኑን የተረዳ ወጣት እንጂ “ፋስት” በሚል ታርጋ የታሸገ የቢዝነስ ተሯሯጭ ለብ-ለብ ትውልድ ብቻ እንዳይሆን አገርና ነገር የገባው ወጣት መገንባት ያስፈልጋል፡፡ባለራዕይ-ለማኝ ዐባይ ሲገደብ የምሰጥህ ሁለት ብር አበድረኝ ይላል::

ያልፈጠርነውን፣ ያላስተማርነውን፣ በአግባቡ ያላነፅነውን ልጅ የሌለ ቅፅል ሰጥተን ብናሞካሸው ረብነት የለውም፡፡ በአናቱ ቅቤ ጣል ያለበት ሹሮ ዓይነት ካፒታሊዝም ኑሮአችን ቅቤ በቅቤ ነው እንደማያሰኝ ሁሉ፤ በእንዲህ ያለ ሥርዓት ውስጥ የሚያድግም ልጅ በአርቲፊሻል የተኳኳለ ከመሆን በቀር ኦርጅናሌ እንደማይሆን እናስተውል፡፡

ከመጠላለፍ ይሰውረን፡፡አደቡን ይስጠን፡፡ በተጠራጠርነው ሁሉ ፍርድ ከመስጠት ያድነን፡፡ እየደጋገምን የምናጠፋው ጥፋት እኛን ራሳችንን ይዞ እንዳይጠፋ መጠንቀቅ ያባት ነው! የምንገባው ቃል መፈፀሙን የሚያረጋግጥልን አንድም ታሪካችን፣ ሁለትም ለራስ መታመናችን ነው! በተግባር የምንሠራው በቃል የምናወራውን ካልመሰለ ዕቅዳችን፣ ስትራቴጂያችን ሁሉ፤ ውሃ የበላው ቤት እንደሚሆን አንርሳ! በታሪክ ያየነው ስህተት እንዳይደገም መጣጣር አዲስ ታሪክ መሥራት ነው!

ናትና ህጻን ልጅዋን ገድሎ የተሰወረው ሰውዬ ትውልዱ ኢትዮጵያዊ ሲሆን በፈረንሳይ ፓሪስ ክርተማ የጎዳና ላይ ተዳዳሪ ነበር:: ሟች ወ/ሮ ክውን ገዳሙ ትባላለች:: ከቤትዋ ወደ ስራ ቦታ ሲመላለሱ ተጠርጣሪውን የዩታል:: በጎዳናው የተጎሳቆለውን ሰው(ጉዳዩ በህግ ስለተያዘ ስሙን እዚህ ላይ አንጠቅሰውም) ስለሚያሳዝናቸው ባለፉ ባገደሙ ቁጥር እጃቸውን ይዘረጉለት ነበር::

ከግዜ በኋላ ከክረምቱ ብርድ እንዲገላገል ሲሉ ይህንን የጎዳና ተዳዳሪ ለግዜው በቤታቸው አስጠጉት:: የአቅማቸውን እየረዱት አብረው ለወራት ኖሩ::

ባለፈው ሳምንት አንድ አስደንጋጭ ክስተት በቤተሰቡ ውስጥ ተፈጸመ:: በችግሩ ያስጠጉት ሰው ከተኙበት በጭካኔ ገድሏቸው አመለጠ::

ወ/ሮ ክውን ገዳሙ የሶስት ልጆች እናት ሲሆኑ በፈረንሳይ ፓሪስ ለረጅም ግዜ ኖረዋል:: የሶስት ልጆች እናትም ናቸው:: ያለአባት ከሚያሳድጓቸውን ሶስት ልጆች ውስጥ አንደኛዋና የሁሉም ታናሽ ከሆነችው ጋር ላይመለሱ ይህችን አለም ባለፈው ሳምንት ተሰናበቱ::

ገዳዩ ጭካኔ በተሞላበት መንገድ በጩቤ ሰነጣትቆ ነው እናትና ልጅን ለህልፈት የዳረገው- እንደ ፈረንሳይ የዜና ምንጭ:: ባጎረሱት እጅ ተነከሱ:: ደግ ባደረጉ ምላሹ ግድያ ሆነ: ለዚያውም አረመኔያዊ ግድያ::

ነብሰ ገዳዩ ለግዜው ተሰውሯል:: የፈረንሳይ ፖሊስ ከኢንተርፖል ጋር በመሆን ጉዳዩን በጥብቅ ይዞታል:: እኛም እየተከታተልን ጉዳዩ ምን እንደደረሰ እናቀርብላችኋላን::
ክንፉ አሰፋ

የተማረ ወይም የእውቀት ባለቤት እንደሆነ የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሕዝብ ክፍል ከወያኔ ጋር የሚደረገው ትግል ሰላማዊ ይሁን ወይስ በትጥቅ ትግል የሚለውን የጦፈ ክርክር ሲያደርግ ሃያ ሁለት ዓመታት ሆነው፤ ዳኛ የሌለበት ክርክር ስለሆነ የመደማመጥ ግዴታ ታይቶበት አይታወቅም፤ ስለዚህም በሁለቱ መሀከል ያለው ልዩነት ግልጽ ሆኖ አያውቅም፤

አንድ፣ ከሁሉ በፊት ሰላማዊ ትግል በሀሳብ ደረጃ መሆኑንና የትጥቅ ትግል ደግሞ በተግባር መሆኑን ለይቶ ለመረዳት ችግር ሆኖ ቆይቶኣል፤ በሌላ አነጋገር ሰላማዊ ትግል በሀሳብ፣ በንግግር፣ በተለያዩ ሀሳብን ለማስለወጥ መቀስቀሻ በሚሆኑ መንገዶች ተቃውሞን መግለጽ ነው፤ በአንጻሩ የትጥቅ ትግል በጠመንጃ ወይም በጉልበት ያለውን የአገዛዝ ሥርዓት ለመለወጥ የሚደረግ ሙከራ ነው፤

ሁለት፣ እንዲህ ከሆነ በሰላማዊ ትግል ለሚያምኑ ሰዎች ያለምንም ጥርጥር በተለያዩ ዓላማዎችና ዘዴዎች ላይ መከራከርና ሀሳብን ማጥራት አስፈላጊ ነው፤ በሰላማዊ ትግል ተግባር አለ ቢባልም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የድጋፍ ወይም የተቃውሞ አቅዋሞችን ከማሳየት አያልፍም፤ አገዛዞች ጃዝ! ብለው ውሻና ፖሊስ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ ሲለቁ የጉልበት ጥርስና ዱላ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ያርፋል፤ ጉዳት ይደርሳል፤ ሰላም ይቃወሳል፤ በሕዝብና በአገዛዙ መሀከል ቂም ይጀመራል።

ሦስት፣ የትጥቅ ትግል ደግሞ በተዋረድ በሚተላለፍ ትእዛዝ የሚፈጸም ግዴታ ነው፤ በትጥቅ ትግል ጉልበተኛ ከጉልበተኛ ጋር፣ ብረት ከብረት ጋር ይጋጠማል፤ የሰው ልጅ ለእርድ ይቀርባል፤ በሕይወታቸው በልተው ያልጠገቡ ምስኪኖች ለጥቂት ሰዎች የሥልጣን ጉጉት ይታረዳሉ፤ ያለቀባሪ በጅብና በአሞራ ይበላሉ፤ ዕድለኞች የሚባሉት እጆቻቸው፣ ወይም እግሮቻቸው ተቆርጠው፣ ወይም ዓይኖቻቸው ጠፍተው፣ ወይም ከዚህ ሁሉ የባሰ ጉዳት ደርሶባቸው በሕይወት የሚቀሩት ናቸው፤ ከነዚህ በሕይወት በቀሩት የጦር ጉዳተኞችና በጦርነቱ ላይ በሞቱት መሀከል የትኛው የተሻለ አንደሆነ የሞቱት ባይናገሩም ጉዳተኞቹ ይናገራሉ፤ ‹የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ!› እያሉ።

አራት፣ ሁለቱ የትግል ስልት ዓይነቶች በባሕርይ የተለዩ ናቸው፤ አንዱ ሌላውን የሚደግፍ አይደለም፤ ሰላማዊ ትግል የትጥቅ ትግልን ለመደገፍ ሰላማዊ የሚለውን ስያሜ መጣል አለበት፤ የትጥቅ ትግልም ሰላማዊ ትግልን ለመደገፍ ትጥቅ የሚለውን ስያሜ መተው አለበት፤ ሰላማዊ ትግልና የትጥቅ ትግል አራማጆች ድል ቢያደርጉ ማን ወንበሩ ላይ እንደሚወጣ ሳይታለም የተፈታ ነው፤ ጠመንጃ የያዘው ሥልጣኑን ሲይዝ ሰላማዊ ትግሉ ይቀጥላል! ያውም ከተፈቀደለት!

በኢትዮጵያ የቅርብ ጊዜ ታሪክ አርበኞች ሳይቀሩ በሩ ተዘግቶባቸው ለደጅ ጥናት እንደተዳረጉ አይተናል፤ መልኩን ለወጥ ቢያደርግም ደርግን ከተፋለሙት ውስጥ በአዲስ አበባና በአስመራ ወንበሮች ላይ ሲወጡ የተሸነፉት ወይ ለወያኔ ገብረው ሎሌነት ገቡ፤ ወይም በአሜሪካ መሽገው ያቅራራሉ፤ ዘመኑ እንዳለፈባቸውም ገና አልተረዱም።

አምስት፣ ሰላማዊ ትግልና የትጥቅ ትግል ሁለቱም ብርቱ ቃል ኪዳንን ይጠይቃሉ፤የቃል ኪዳናቸው ልዩነት አንዱ እስከሞት ለመታገል፣ ሌላው ደግሞ እስከመግደልና እስከመሞት ለመታገል መሆኑ ነው፤ ለሰላማዊው ትግል ከፍተኛ መንፈሳዊ ወኔ የሚያጎናጽፈው ለመግደል ያለው ተቃውሞ ነው፤ ሕይወትን ለማልማት ሕይወትን መቅጠፍ የአስተሳሰብም የመንፈስም ጉድፍ ያለበት ሥራ ነው።

የሰላማዊ ትግል ዋናውና ቀጥተኛው ተልእኮ ሕዝብን ለሥልጣን ባለቤትነት ማብቃት ነው፤ ሥልጣንን ለመያዝ አይደለም፤ ስለዚህም ኢላማው ሕዝብ ነው፤ በሥልጣን ወንበሩ ላይ ያሉት የሰላማዊ ትግሉን የሚቃወሙት በሕዝብ ዘንድ ተሰሚነትና ተቀባይነት እንዳያገኝ ለማድረግ ነው፤ ሰላማዊ ትግሉ የሚያተኩረው በሕዝቡ ጆሮ፣ አእምሮና ልብ ላይ ነው፤ አገዛዙ በበኩሉ ጸጥ-ለጥ ብሎ የሚገዛለት ሕዝብ እውቀቱ ዳብሮ፣ መብቶቹን ሁሉ ተገንዝቦ፣ በሕግ ለሕግ እንጂ ለሰው አልገዛም በማለት ልቡ እንዳይሸፍት አፈናውንና ማነቆውን በማጠናከር እያደነቆረ ለመግዛት ይፈልጋል፤ የሰብአዊ መብቶችን የሚያስተምሩና በአገዛዙ አካላት የሚፈጸሙትን የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን የሚያጋልጡ ድርጅቶችን ማዳከም ወይም ማጥፋት ለአገዛዙ አስፈላጊ የሚሆነው ለዚህ ነው፤ ኢሳት የሚባለው የቴሌቪዥንና የራድዮ ፐሮግራም ለወያኔ የውስጥ እግር እሳት የሆነበት ለዚህ ነው፡፡ በሰውነት ደረጃ ሕዝቡ መብቶቹን ሁሉ እንዲያውቅና እንዲረዳ ማድረግ፣

በዜግነት ደረጃ ሕዝቡ ለሥልጣን የሚያበቃውን የዜግነትና የፖሊቲካ መብቶች እንዲያውቅና እንዲረዳ ማድረግ፣ ሕዝቡ የሰውነትና የዜግነት መብቶቹን ተገንዝቦ በአገዛዝ ስር አልተዳደርም የማለት መንፈሳዊ እምቢተኛነት እንዲያድርበት ማድረግ፣ በግልጽ ጭቆናን የሚጠላና ለመብቶቹና ለነጻነቱ በቆራጥነት የሚቆም ሕዝብ እንዲፈጠር ማበረታታት፣ መብቶቹንና የሥልጣን ባለቤትነቱን የተረዳና ከጭቆና ጋር የተጣላ ሕዝብ በፖሊቲካ መስመር ቡድኖችን እየፈጠረ እንዲደራጅ ማድረግ፣ ያወቀና የነቃ፣ በፖሊቲካ መስመር የተደራጀና ማናቸውንም ዓይነት ጭቆና የሚጠላ ሕዝብ ለማንም ጉልበተኛ የማይንበረከክ ሕዝባዊ ኃይል እንዲሆን መጣር፣

የትጥቅ ትግል ዋናውና ቀጥተኛው ተልእኮ በሥልጣን ላይ ያለውን አገዛዝ አውርዶ ወንበሩን ለራሱ ለመውሰድ ነው፤ ይህንን ሲያደርግ ሕዝቡን ወደጎን ትቶ ወይም ዘልሎ ነው፤ ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ በጠመንጃ ሥልጣን የሚይዙ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሥልጣኑን ለሕዝብ እናስረክባለን፤ ትክክለኛ ምርጫ እናካሂዳለን በማለት ሕዝቡን በተስፋና በጠመንጃ ይዞ ነው፤ ነገር ግን ሥልጣንን ሕዝብ ለፈቀደው አስረክበው ከቤተ መንግሥት ሲወጡ አናይም፤ ሲሸሹ ወይም ሬሳቸው ሲወጣ እንጂ።

ብዙውን ጊዜ የማይታሰብ ወይም ብዙዎች የሚዘነጉት የሁለቱ ትግሎች የገንዘብ ወጪ በጣም ከፍተኛ ልዩነት ያለው መሆኑን ነው፤ ሰላማዊ ትግል በሕይወትም፣ በንብረትም፣ በመሣሪያም በዝግጅትም የሚያስከፍለው ዋጋ ከትጥቅ ትግል ጋር ሲወዳደር በጣም አነስተኛ ነው።

ስለዚህም በሁለቱ በተለያዩ ስልቶች አራማጆች መሀከል የሚደረግ ክርክር ምን ዓይነት ነው? የሰላማዊው የመጀመሪያ ደረጃ ኢላማው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ የትጥቅ ትግል የመጀመሪያ ደረጃ ኢላማው የወያኔ አገዛዝ ነው፤ በሌላ አነጋገር በሰላማዊ ትግል ሕዝቡ በሰላማዊ ትግል ትንሽም ቢሆን የነጻነትን አድማስ ለማስፋት እንዲችል ድፍረትን በማስተማር በኩል የማይናቅ አስተዋጽኦ ቢያደርግም አገዛዙን የመነቅነቅ ኃይል ገና አላዳበረም፤ አንድም ውጤት አላሳየም፤ የትጥቅ ትግሉ ከፉከራና ከሽለላ እስካሁንም አልወጣም፤ የሰላማዊ ትግል ዓላማ ሕዝቡ መብቶቹን እንዲያውቅ ለማንቃትና ለመብቶቹ እንዲታገል የሚያስችለውን ብቃት ለማስጨበጥ ነው፤ ስለዚህም ዘዴው በሕዝቡ ላይ ነው፤ የትጥቅ ትግሉ ዘዴ አገዛዙን በጉልበት ገልብጦ በዚያው ባልተለወጠ ሕዝብ ላይ ሌላ አገዛዝ ለመመሥረት ነው።

በኢትዮጵያ ለውጥ እናመጣለን የሚሉ ሁሉ የቆሙበትንና የቆሙለትን ዓላማና ዘዴ በግልጽ ተገንዝበው ካልተሰለፉ በተንፈራጠጠ አስተሳሰብ የተባበረ ተግባር ሊገኝ አይችልም።

EMF

Image

Image

ምንሊክ ሳልሳዊ፦በተመሳሳይ ቀን የወያነ ባለስልጣኖች አለማየሁ አቶምሳን በሞት ሲነጠቁ የሻእቢያ ባለስልጣኖች ደግሞ ከፍተኛ የጦር አዛዣቸውን እና ታጋይ መጀር ጀነራል ገብረዝገር “ዉጩ” አንደማሪያምን በሞት ተነጥቋል።

አቶ አለማየሁ በባንኮክ በከፍተኛ ውጪ ሲታከሙ የሞቱ ሲሆን የሻ እቢያው ጀነራል ግን በአስመራ ከተማ በህክምና ሲረዱ ቆይተው አርፈዋል። አቶ አለማየሁ አቶምሳ ከሕወሓት ሰራሹ ኦሕደድ ጋር ተቀላቅለው ታጋይ የነበሩ(ማረጋገጫ አልተገኘም) ሲሆን ጀነራል ገረዝገር ሻ እቢያ ከደርግ ጋር ባደረገው ጦርነት ከ1971 ጀምሮ የተሳተፉ ታጋይ እንደነበሩ ከአስመራ የወጡ ዘገባዎች ያመለክታሉ። ምንሊክ ሳልሳዊ

አቶ አለምነው መኮንን በአማራው ህዝብ ላይ ያዘነቡትን ጸያፍ ስድብ ተከትሎ ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ የገባው ብአዴን፣ በክልሉ ፕሬዚዳንት በአቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ በራሳቸው በአቶ አለምነው መኮንን እንዲሁም በብአዴን ሊቀመንበርና በምክትል ጠ/ሚንስትር ደመቀ መኮንን አማካኝነት መግለጫ ቢሰጠም፣ ህዝቡን ለማሳመን ባለመቻላቸው፣ በወቅቱ በስብሰባው ላይ የተገኙ ጋዜጠኞችና ሌሎች ተወያዮች ቀርበው አቶ አለምነው አልተናገሩም እያሉ እንዲያስተባብሉ እየተደረገ ነው።

ከአስተማማኝ የደህንነት ምንጮች በተገኘው መረጃ መሰረት ደግሞ መረጃውን ያቀበሉትን ሰዎች ለማወቅ በወቅቱ የነበሩትን ጋዜጠኞች፣ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊዎችና የደህንነት ሰራተኞች ስልክ በመጥለፍ ተጨማሪ ክትትል እያደረጉ ነው። ይሁን እንጅ መረጃው አስቀድሞ የደረሳቸው የደህንነት ሰዎች ማንኛውንም በስልክ የሚያደርጉትን ግንኙነት በማቆማቸው የተፈለገው ውጤት ሊገኝ ባለመቻሉ ተጨማሪ ራስ ምታት መፍጠሩ ታውቋል።አቶ ደመቀ መኮንን ተቃዋሚዎች ልማቱን ለማደናቀፍ የፈጠሩት የኮምፒዩተር ቅንብር ነው ቢሉም የብአዴን አባላት ሳይቀሩ በሊቀመንበሩ ንግግር መበሳጨታቸውን ተናግረዋል። በሚቀጥለው አርብ በሚደረገው የአማራ ክልል ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ጉዳዩ ይነሳል ተብሎ ይጠበቃል።

አንድነትና መኢአድ በባህርዳር ያደረጉት የተቃውሞ ሰልፍና ለተቃውሞ የወጣው ህዝብ ብዛት ያስደነገጣቸው የብአዴን አንዳንድtአመራሮችና አባላት፣ አቶ አለምነው በይፋ ህዝቡን ይቅርታ ይጠይቁና ይህ ምእራፍ ይዘጋ በማለት እየጠየቁ ሲሆን፣ ዋናዎቹ አመራሮች ግን ጉዳዩ የአንድ ሰሞን ጫጫታ ከመሆን አይዘልም በማለት የሌሎችን አስተያየቶች ሊቀበሉ ፈቃደኞች አልሆኑም።

በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች ወላይታ ሶዶ 18 ሰዎች ካለፍርድ ቤት ትእዛዝ ጨለማ ቤት ታስረዋል::
“ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገር ድረስ መጥታችሁ ቅስቀሳ ለማካሄድ መሞከራችሁ በጣም ደፋሮች ናችሁ! ከዚህ በኋላም ወላይታ ላይ እንዲህ አይነት ነገር እንዳትሞክሩ!” የወላይታ ሶዶ ፖሊስ ማስፈራሪያ ለሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች

ምንሊክ ሳልሳዊ:- የጠቅላይ ሚኒስትር ተብየው ሃይለማርያም ደሳለኝ ምንጭ ናት በምትባለው በወላይታ ሶዶ ከከፍተኛ ደረጃ የሰብኣዊ መብት ጥሰቶች እየተፈጸሙ መሆኑን ነዋሪዎች አጋለጡ::ነዋሪዎቹ እንዳሉት ካለምንም ምክንያት የሚያፍኑ የሚያስሩ የሚገርፉ እና ከፍትህ እና ፍርድ ቤት በላይ የሆኑ ትናንሽ ቡድናዊ መንግስታት እና እንዳሻቸው በህዝቡ ላይ የሚፈነጩ ካድሬዎች የወላይታን ህዝብ በስቃይ እና በሰቆቃ ውስጥ እያኖሩት መሆኑን ነዋሪዎቹ አማረው ተናግረዋል::

ባለፈው ሳምንታት ውስጥ እንኳን ከተያዙት የወላይታ ነዋሪዎች መካከል አቶ አየለ ሃሚሶ የሚባል የከተማውን የፍርድ ቤቶች ፕሬዚዳንት እና ዳኛ ደብድባችኋል ተብለው ካለምንም ማስረጃ 18 ሰዎች ተይዘው ላለፉት አስረ አምስት ቀናት ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ በጨለማ ቤት ታስረው ይገኛሉ::እነዚህ እስረኞች የከተማው ፖሊስ አዛዥ ኢንስፔክተር ሌሊሼ ኦላ እና ግብረበሮቹ ከፍተኛ ድብደባ እየተፈጸመባቸው ሲሆን እንዲሁም ደብዳቢዎቹን ጭናችሁ አድርስቹሃል የተባሉ የባጃጅ ሹፌሮች በቁጥጥር ስር ውለው እየተገረፉ መሆኑን በስቃይ ላይ ያሉት እስረኞች ተናግረዋል::

ይህ በእንዲህ እንዳለ በህጋዊ መንገድ የተመዘገበውን የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችን በሽብርተኛነት እና ህገወጥ የጦር መሳሪያ ይዛቹሃል በማለት እንግልት እና መንግስታዊ ሽብር በከተማው የፖሊስ አዛዥ እና ግብረአበሮቻቸው የተፈጸመባቸው ሲሆን በሻንጣዎቻቸው ላይ ፍተሻ አድርገው ምንም የጦር መሳሪያ እንዳላገኙ እና “ወላይታ ለመግባት ምንም አይነት ፈቃድ ከማንም አንጠብቅም ምክንያቱም አገራችን ነው” በማለት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ቢመልሱም “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገር ድረስ መጥታችሁ ቅስቀሳ ለማካሄድ መሞከራችሁ በጣም ደፋሮች ናችሁ! ከዚህ በኋላም ወላይታ ላይ እንዲህ አይነት ነገር እንዳትሞክሩ!” የሚል ዛቻና ማስፈራሪያ
አድርሰውባቸዋል::

ዛሬ የካቲት 26 2006 “አሁን መሄድ ትችላላችሁ” ብለው ከአዲስ አበባ የሄዱትን ሶስቱን የሰማዊ ፓረቲ አመራሮች 1ኛ/ አቶ ጌታነህ ባልቻ 2ኛ/ አቶ ብርሃኑ ተ/ያሬድ 3ኛ/ አቶ ይሁን አለሙ ሲለቁዋቸው ከሀዲያ ጀምረው የሰሯቸውን ስራዎች የያዙበትን ሰነዶች፤ቃለ ጉባኤዎች እና ሁለቱን የወላይታ ተወካዮችን /አስተባባሪዎችን/ እስካሁን ያለቀቋቸው ሲሆን ስለ ንበረታችሁ የምናውቀው ነገር የለም በማለታቸው ንብረቶቻቸውን ሳይረከቡ ወደ አርባምንጭ መንቀሳቀሳቸው ታውቋል::

የታሰሩት የሰማያዊ ፓረቲ የወላይታ አስተባሪዎች ባይፈቱም፤ የተወሰዱባቸው ንብረቶች ባይመለሱላቸወም ሰራው መቀጠል ሰላለበት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ወደ አርባ-ምንጭ ተንቀሳቅሰዋል፡፡
ነገ የአርባ ምንጭ ሰራቸውን እንዳጠናቀቁ ወደ ወላይታ ሶዶ ከትማ ተመልሰው የታሰሩትን የሶዶ ከተማ አስተባባሪዎችን ለማስፈታት ትግሉ የሚቀጥል ሲሆን ንበረታቸውንም የማስመለሰ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል!!
ትላንትና የካቲት 25 2006 በሶዶ ከትማ ላይ ያደረጉዋቸው ሰበሰባዎች https://www.facebook.com/blueparty.ethi … =notify_me ይህንን ይመሰል ነበር፡፡ምንሊክ ሳልሳዊ

እስከዛሬ ብዙ ቀልዶችን ሰምቻለው አንደዚህ ግን ያዝናናኝ ቀልድ የለም አንድ የቀድሞ የግብጽ ጀነራል ኢትዮጵያ የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታን የማታቆም ከሆነ እናፈነዳቸዋለን አሉ ለአንድ የቴሌቭዥን ጣቢያ በሰጡት ቃለ ምልልስ ኢትዮጵያ የህዳሴው ግድብ እንድታቆም ሶስት አማራጮች አሉ ብለዋል።

የቀድሞው የግብጽ ጀነራል በቀዳሚነት ያስቀመጡት አማራጭ በኢትዮጵያ ፣በሱዳን እና በግብጽ 20 ሚልዮን የሚደርስ የሙዝ እና የዛፍ ችግኝ በመትከል እና የዝናብ ሁኔታው እንዲስተካከል በማድረግ እና አማራጭ በመስጠት ኢትዮጵያ ግድቡን የምታቆምበትን መንገድ ማመቻቸት ነው ብለዋል።

ሁለተኛው አማራጭ የቀድሞ የግብጽ ንጉስ ሱልጣን አብዱል ሃሚድ የኢትዮጵያን አንድ ሶስተኛ መሬት ያስተዳድር ስለነበር ይህን መሬት አንዲሰጠን መጠየቅ ነው ያሉት የቀድሞ ጀነራል የዩጋንዳ አንድ ሶስተኛ መሬትም የግብጽ ንብረት እንደሆነ ተናግረዋል።

ይህንንም ለማድረግ ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ እንደተዘጋጁ ነው የሚናገሩት። ሁለቱ አማራጮች የማይሰሩ ከሆነ ግን « በመሬታችን መሞት የለበንም መሞት ካለብንም ግድባቸው ስር ነው መሞት ያለብን ስለዚህ እዛው ሄደን ልንፈነዳቸው ይገባል በመሆኑም ኢትዮጵያ ከሶስቱ አማራጮች አንዱን መምረጥ አለባት» ብለዋል።
እንኳንስ ለሙቅ ለገንፎም አልደነግጥ አለ የሃገሬ ሰው!! አፈነዳለሁ በሎ ፈነድቶ የአሞራ እራት መሆን እንዳለ አያውቁም እንዴ ጀነራል? ቂቂቂ ቂቂቂ ቂቂቂ ቂቂቂ በነገራችን ላይ ጀነራል ሶስቱም የኛ ምርጫ አይደሉም የኛምርጫ ወንዛችንን መገደብ ነው…እኔ የሚገርመኝ ኧረ ግብፅ በጣም አበዛችው
አንድ ሰሞን ክቡር ጠ/ሚር መለስ ዜናዊ እንዲህ ሲሉ ሰምቼ ነበር ” ለሚያስፈራራክ ሰው መፍትሄው አለመፍራት ነው ” ሳስበው ሳስበው ይህ ሰው ጅል እንጂ ጄነራል አይደለም!! ቂቂቂ ቂቂቂ ደስ የሚለው ነገር ጅነራሉም ሆኑ አንዋር ሳዳት አንድ አይነት እምነት አላቸው እዚያው ሄደን እንሙት !! እኛ መግደል መገዳደል ሰልችቶናል ሁላችንም በህይወት እንኑር ነው አቋማችን እግድህ የኛ መሬት ለባዐዳን መቀበርያ ይመች ይመስል የአሁኑ ትውልድም እንደ ድርቡሽ እዚያው እንሙት ቢያንስ እንደ ጣልያኖቹ የገዳዮችና የሟቾች ሃውልት በኢትዮጵያ ምድር ይኑረን አጥንታችን በኢትዮጵያ መሬት ካልተቀበረ የሞትን አይመስለንም ካሉ ባንወደውም ባንፈልገውም ሙትን ለመቅበር ከሟቹ ይልቅ ጉልበትና አቅም ይጠይቃልና ለዚያው መዘጋጀት ነው አንድም ሞት የናፈቃቸው ግብጻውያንን እዚየው ጣሕሪር አደባባይ ላይ ሞታቸው እንድከናወን መጸለይ ነው ካልሆን ግን ምን ይደረግ ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደር ? ይስሙኝ እማ ጀኔራል በአባይ የመጣ እንኳን የኢትዮዻያ ወጣት እማማ አያቴ ትዘምታለች.ቂቂቂ እንዳዉም አረፈዳችሁ ቂቂቂቂቂቂ ቂቂቂ
ጀነራል እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ”ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፥ ኃያልም በኃይሉ አይመካ፥ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ ነገር ግን የሚመካው። ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፥” ይላል እግዚአብሔር።
ትንቢተ ኢሳይያስ 19;1-10 ላይ
ስለ ግብጽ የተነገረ ሸክም። እነሆ፥ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እይበረረ ወደ ግብጽ ይመጣል፤ የግብጽም ጣዖታት በፊቱ ይርዳሉ፥ የግብጽም ልብ በውስጥዋ ይቀልጣል።
2፤ ግብጻውያንን በግብጻውያን ላይ አስነሣለሁ፤ ወንድምም ወንድሙን፥ ሰውም ባልንጀራውን፥ ከተማም ከተማን፥ መንግሥትም መንግሥትን ይወጋል።
3፤ የግብጽም መንፈስ በውስጥዋ ባዶ ይሆናል፥ ምክራቸውንም አጠፋለሁ፤ እነርሱም ጣዖቶቻቸውን በድግምት የሚጠነቍሉትንም መናፍስት ጠሪዎቻቸውንም ጠንቋዮቻቸውንም ይጠይቃሉ።
4፤ ግብጻውያንንም በጨካኝ ጌታ እጅ አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ጨካኝ ንጉሥም ይገዛቸዋል ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር።
5፤ ውኆችም ከባሕር ይደርቃሉ፥ ወንዙም ያንሳል ደረቅም ይሆናል።
6፤ ወንዞቹም ይገማሉ፥ የግብጽም መስኖች ያንሳሉ ይደርቃሉም፤ ደንገልና ቄጤማ ይጠወልጋሉ።
7፤ በዓባይ ወንዝ ዳር ያለው መስክ በዓባይም ወንዝ አጠገብ የተዘራ እርሻ ሁሉ ይደርቃል፥ ይበተንማል፥ አይገኝምም።
8፤ ዓሣ አጥማጆቹ ያዝናሉ፥ በዓባይም ወንዝ መቃጥን የሚጥሉት ሁሉ ያለቅሳሉ፥ በውኆችም ላይ መረብ የሚዘረጉት ይዝላሉ።
9፤ የተበጠረውንም የተልባ እግር የሚሠሩ፥ ነጩንም ልብስ የሚሠሩ ሸማኔዎች ያፍራሉ።
10፤ ደገፋዎችዋም ሁሉ ይሰባበራሉ፥ የደመወዘኞችም ነፍስ ትተክዛለች።

ይስሙኝ እማ ጀኔራል በነገራችን ላይ ይኼን ግድብ ማፈንዳት አይደለም መገላመጥ በነፍስ ያወራርዳል፡፡ግድቡ የኢህአዴግ ሳይሆን የኢትዮጵያ ህዝብ ነው፡፡ ኢጣሊያንን ያየ በእሳት አይጫወትም” አለች እማማ አያቴ . ቂቂቂ ቂቂቂ ቂቂቂ አይ አቅምን አለማወቅ ያሳዝናል የጦር መሳሪያ እስከ አፍንጫ መታጠቅ እንዲህ የሚያስፈነጭ መስሏቸው ከሆነ ከጣሊያን ይማሩ፡፡ጦርነት ሚጠይቀው ወኔና አላማ ነው ፡፡እንኳን ለግድባችን ….ይሞታል፡፡ታሪክ ጠይቁ የማን ልጆች እንደሆንን የሚኒልክ እና የቴድሮሥ አንፈራም ነገርዬው ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ አይነት ነው ግድቡ ስር ለመሞት መጀመሪያ መድረስ ይጠይቃል፤ ማፈንዳቱ ሳይሻላችሁ አይቀርም? ግን ልታፈነዱ ስትመጡ ልትፈነዱ አንደምችሉ አስባችሁ ግቡ! አገሪቱ ኢትዮጵያ, ህዝቡ ደግሞ የአድዋ ባለ ታሪክ ጀግና አንደሆነ ለአፍታም አንዳትዘነጉ! ቀልደኞች ቂቂቂ!! ጋሸ ጀነራሉ ወግ ከወግነቱ አልፎ አያውቅም ሞያ በልብ ነው ካወራህ ይበቃህል ኢትዮጵያና ህዝቦችዋ ለጠላት የተንበረከኩበት ዘመን የለም የታሪክ አሻራውን ማየት ከፈለክ ሜዳውም ፈረሱም ይህው። ጋሸ ጀነራሉ እንደዚህ አይነት ቀልድ ግብፅም ጀመረች እኛ ማን እንደሆን አታቅም እንዴ? ካላወቀች ጣሊያንን ትጠይቅ! ጀግኖቹ ኢትዮዽያኖችነን!!! ከእሳት እንዴት ችላ ትጠጋለች!! እኛ እኮ ለሚጠሉን እሳት ነን ለሚወዱን ደግሞ ዉሀ ነን.. እ!

ስሙኝማ በነገራችን ላይ አረብ ሲባል የሻገተና የአስተሳሰብ ደኃ ነው፡፡ እንደልማዳችሁ እናፈነዳለን ብልችሁ ስትነሱ እራሳችሁ ላይ አፈንድታችሁ ታልቃላችሁ፡፡ አሁን የጨዋታው ህግ ተቀይሯል፤ እንኳንስ የኃይል እጥረት እያለብን ይቅርና ቢተረፈረፈንም ግድቡ አይቆምም ፡፡ ደግሞ እንዳይገርማችሁ ፤ ይህ ከአራቱ ግዶቦች የመጀመሪያው ነው 3ቱ በቅርብ ጊዜ በቅደም ተከተል ግንባታ ይጀመራል፡፡ ስለሆነም ውኃችን ነዳጃችን ነው ፡፡ ነዳጂ በነፃ አለ እንዴ??? በነገራችን ላይ ጀኔራል ሙዝ እና ችግኙም አሪፍ ሀሳብ ነው። ከግድቡ በኃላ ወደዛም እንዘምታለን ቂቂቂ ቂቂቂ በነገራችን ላይ ጀኔራል ይልቁንም ለብዙ ሺህ አመታት ያለከልካይ የአባይን ውሃ ተጠቅመዋል ስለዚህ ለኢትዮጵያ በርካታ በሊዮን ዶላር ሊከፍሉ ይገባቸዋል!!!!
አሁን ነው መበቀል አረብን እስካሁን በትንሽ ሳንቲም የአበሻን ጉልበት የበዘበዙበት ሳያሳቸው በዚም መጡ ይሄ ግድብ ክብራችንን ከፍ የሚደርግልን ነው በዛውም ልክ ግድቡ ላይ ጥቃት ደርሶ ማለባበስ በቁም እንደመሞት ነው ለአገራችን ክብር መንግስት ራሱን ሊዘጋጅበት እና በማንኛውም እንቅስቃሴ አፀፋዊ መልስ ሊሰጥ ይገባል የስካሁኑ ውርደት በአረቦች ይብቃ ካለበለዚያ ሀገርንም በማስደፈር እስካሁን ከነበሩት መንግስት ቀዳሚው የትውልድ ተወቃሽ መሆኑ ማይቀር ነው እናም መንግስት በሁሉም ነገር አፀፋዊ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆን ይገባል፡

ስሙኝማ ነገርዬው ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ አይነት ነው፡፡ ግብፆች ከድርድር ውጪ የጦርነት አማራጭ ያላቸው አይመስለኝም፡፡ የተያያዙት ተራ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ነው፡፡ ያው ማስፈራራት ነው፡፡ ቢሆንም በደካማ ጎናችን አይጠቀሙም ማለት አይታሰብም፡፡ የግብፅ ግብረሰናይ ድርጅቶችም ሆኑ ማናቸውም የግብፅ መሰረት ያላቸው የኢንቨስትመን ስራዎች ላይ ጥብቅ ቁጥጥር ካልተደረገ ሊጎዱን ይችላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ብቻ ሊሰራ የሚችል ወታደራዊም ሲቪል ደህንነት ተቋም ሊመሰረት ይገባል፡፡ መስራት ከባድ ነው፡፡ ማፍረስ ቀላል ነው፡፡ የቁማር ጨዋታው ውጤት ግልጽ ስላይደለ መዘጋጀቱ አይከፋም፡፡ በድንበር አካባቢ ያለንን የፀጥታ አጠባበቅ ማጥበቅም ግድ ይለናል፡፡
ግድቡ ተዓምር ባያመጣልን እንኳ ግብፅ ለዘመናት ያፈራረሰችንን ማካካሻ ስለሚሆን ለእኔ ልዩ ትርጉም አለው፡፡ ለብዙ ላልተገለፁ ነገሮችም መሰረት ይሆናል፡፡ አይደለም 6ሺ 200 ሜጋ ዋትም ካመነጨ በድል አድራጊነት እንዳጠናቀቅን እቆጥራለሁ፡፡የግብፅን የውስጥ መተራመስ ፈጣሪ ለኛ ብሎ ያደረገው እንደሆነስ ማን ያውቃል! ባይሆን ኖሮ የሚተኙልን አይመስለኝም፡፡ በዚህ ምስቅልቅል ጊዜ ይህን ያህል ከተንፈራገጡ ደህና ቢሆኑ ውጤቱን ገምቱ…መንግስትም ለማናቻውም ማስፈራራት ተመጣጣኝ ምላሽ መስጠት ይኖርበታል፡፡ ግድ ነው፡፡
ይስሙኝ እማ ጀኔራል በትምቢቱ ኢሳያስ መዝ67:31 ኢትዮጵያ ላይ ጦርን እንዳታነሱ ትደቃላችሁ ብሏል።በደንብ ይወቁን ይምጡ ሙዝ እንዳሉ የርሳስ ሙዝ በልተው ይሄዳሉ።
ቂቂቂ ቂቂቂ
ህዝብ ሆይ ስማ እንደወርቅ የነጠረ እንደ ብር የነጣ ሀበሻዊ ማንነትህ በሙዝ ተቀይራል እና መሳሪያም ያለህ መሳሪያ ጀገሪያም ያለህ ጀገሪያ አንካሴም ያለህ አንካሴ እነኚህ የሌላችሁ ወኔአችሁን ይዛችሁ ወደ አባይ ውጡ ይህን ማድረግ ያልቻለ ሀበሻ ቢኖር እንጣላለን ማርያምን!!!!!!!
አሁንስ ትግስቴ እያለቀ ነዉ ያአባቴን ak-47 መሳሪያ ይዤ ልሸልል ነዉ ያበጠ ይፈንዳ ምነዉ ሸዋ
አረ ጎራው አረ ጎራው ንቡ ወለደና ቀፎውን ጨነቀው፣
ማር ብቻ መስሎታል መርዙን አላወቀው፣
የማን ዘር ነኝና ከማስ ተወልጄ
ሚኒልክ ያወረሰኝ ዛሬም አለ በጀ።
ዘራፍ ዘራፍ የማንን ሀገር ማን ይነካታል፣
ካለ ሀበሻ ያስከብራታል።
የማን ቤት ጠፍቶ የማን ሊበጅ፣
የአውሬ መውለጃ ይሆናል እንጂ።
ዘራፍ ዘራፍ!!! ዘራፍ!!! ዘራፈ!!
የምኒሊክ ልጅ ነኝ የበላይ የዛ ሳተና
ለጣልያንም ያልተኛ ቆራጡ ጀግና እኔነኝ ያለ ይሞክረኛ !!! ዘራፍ ዘራፍ!!!ተተተተተተተተተ ”ኢትዮጵያ ታበፅእ እደዊሀ ሀበ እግዚአብሄር
እንግዲ እነሱ በሚፈልጉት አማራጭ መሄድ ይችላሉ መብታቸው ነው። እኛ ኢትዮጵያዊያን ያለን አንድ እና አንድ ነው ያለን ያም የኃያላን ኃያል የነገስታት ንጉስ በረዶ የሚያዘንብ ፈርኦንን ከነሰራዊቱ በባህር የጣለ ድንቅ መካር እና ኃያል አምላክ ነው እሱም እጃችንን ዘርግተን ለምነን ከኛ ጋር ነው ስለዚህ ቀድመን አሸንፈናቸዋል
እኛስ እንሙት ችግር ብርቃችን አይደለምና መጪው ትውልድ ግን እኛ ያየነዉን ችግር እኛ ያለፍንበትን የድህነት ህይወት መቅመስ የለበትም ብሔር ሀይማኖት ሳይለየን ሁላችንም በአንድነት ለመጪው ትውልዳችን መስዋት ከፍለን ማለፍ አለብን ስም አይሞትም ታሪክም አይሞትም::እነሱ ያውሩ እኛ እንሰራለን ©2014 ነቆራ እና ሌሎችም ወጎች ከ Love on The way

ኢህአዴግ የአንድነት ፓርቲ ኃይሎች በአደረጃጀቴ ሰርገው ገብተተዋል በሚል ግምገማ ለጀምር መሆኑ ታወቀ፡፡ የአዲስ አበባ ኢህአዴግ ጽ/ቤት የአንድ-ለ-አምስት የአደረጃጀት አመራሮች በተለያዩ ክፍለ ከተማዎች የሚገኙ የአንድ-ለ-አምስት የአደረጃጀት አመራሮችን በመሰብሰብ “አንድነት ፓርቲ የአንድ-ለ-አምስት አደረጃጀታችን ውስጥ አስርጎ ያስገባቸው ኃይሎች በጊዜ በግምገማ ካልተራገፉ ቀጣዩ ምርጫ ከቁጥጥር ውጪ እንደማይሆን ማንም እርግጠኛ መሆን አይችልም፡፡” ማለታቸውን በስብሰባው ላይ የተሳተፉ የፍኖተ ነፃነት ምንጮች ተናግረዋል፡፡

ምንጮቹ ጨምረው እንደተናገሩት ኢህአዴግ የአንድ-ለ-አምስት አደረጃጀቱን የሚያስተባብሩ ከፍተኛ ካድሬዎችን አንድ-ለ-ሰላሳ ማደራጀት መጀመሩን ተከትሎ አንድነት ፓርቲ አስርጎ ያስገባቸው ኃይሎች አሉ በመባሉ ካድሬዎች እርስ በእርስ መሰላለል እና አለመተማመን ጀምረዋል፡፡ ይህ በካድሬዎቻቸው መካከል የተጠፈጠረው ትርምስ ያሰጋቸው የኢህአዴግ የአዲስ አበባ ጽ/ቤት አመራሮች ለክፍለ ከተማ አመራሮቻቸው አንድነት ሊይዝብን የሚችለው 30 በመቶ የሚሆነውን ህዝብ ነው የተቀረውን በኮንዶሚኒየም ፣ በአነስተኛ ጥቃቅንና በየአንድ-ለ-አምስት አደረጃጀት ይዘነዋል ብለዋቸዋል፡፡ ለፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ መረጃ የሰጡት የስብሰባው ተሳታፊዎች 750ሺ የኮንዶሚኒየም ተመዝጋቢ፣ 30ሺ የኮንዶሚኒየም እጣ ተጠባባቂዎች ኢህአዴግን ነው የሚመርጡት በሚል ከመድረክ የቀረበው መደምደሚያ እንዳላሳመናቸውም ተናግረዋል፡፡

ጉዳዩን በሚመለከት ለፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ ከአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ የደረሰው ዶክሜንት እንደሚያስረዳው ፓርቲው የአዲስ አበባ አደረጃጀቱን ኢህአዴግ በዘረጋው ልክ 138 ያደረሰ ሲሆን በአሁኑ ጊዜም የወረዳ ደረጃና የሴል አደረጃጀቶቹን በኢህአዴግ የአደረጃጀት ቁጥር ልክ የማድረግ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ያመለክታል፡፡

በብኣዴን ካድሬዎች መካከል የተነሳው ፍጥጫ የሕወሓት አመራሮች በሃይል ሊፈቱት ይችላሉ የሚል ስጋት ጨምሯል።
ሕወሓት በአማራው ክልል አዲስ የፓርቲ አደረጃጀት ጥርነፋ ሊደርግ ነው።

ምንሊክ ሳልሳዊ ፤ የብኣዴን ካድሬዎች ድርጅታቸውን እና አመራራቸው ላይ የሚታየውን ጉዳይ በተመለከተ የፖለቲካ ጥያቄዎች ማንሳታቸውን ተከትሎ ከሕወሓት አሽከር ከሆኑት ጋር በስብሰባ ላይ በተፈጠረ አለመግባባት ስብሰባው እንደተበተነ ታውቋል:: በሕወሓት እና በብኣዴን መካከል ልዩነቶች የሚፈጥሩ ሁኔታዎች ተከስተው አሁንም በስፋት ቀጥለው ይገኛሉ::የተለያዩ ነባር የብኣዴን ካድረዎችን በሰብብ አስባብ የሚያንጠባጥበው ሕወሓት አሁንም አሽከሮቹን አሰማርቶ በድርጅታቸው ውስጥ ለውጥ እንዲደረግ እና የሕወሓት ደባልነትና ፖለቲካ ጥገኝነት እንዲያበቃ የጠየቁትን ወደ ገደል ለመግፋት አየተሯሯጠ ነው::

ባለፉት ሳምንታት በባህር ዳር እና በአዲስ አበባ የተጠሩ ስብሰባዎች በሕወሓት አሽከሮች እና በለውጥ ጠያቂዎች መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ስብሰባው ሲበተን …ለሁለተኛ ጊዜ የተጠራው ስብሰባ በከፊል ካድሬዎቹ ስላልመጡ ለሚመጣው ሳምንት የተላለፈ መሆኑን ታውቋል::በሕወሓት አሽከሮች እና በብኣዴን ለውጥ ፈላጊ ካድሬዎች መካከል የተነሳው ፍጥጫ የሕወሓት አመራሮች በሃይል ሊፈቱት ይችላሉ የሚል ስጋት ጨምሯል::

አዲስ በወጣው እቅድ መሰረት በአማራው ክልል በድጋሚ አዲስ የፓርቲ አደረጃጀት ጥርነፋ እንደሚደርግ እና በዚህ መካከል አስቸጋሪ እና አድመኞች የጸረ ሰላም እና የጸረ ሕዝብ ሃይሎችን የመደምሰስ እንዲሁም በአዲሱ የፓርቲ አደረጃጀት ውስጥ አስፈላጊው ጥቅማጥቅሞችን ለአዳዲስ አባላት መስጠት የሚል ይገኝበታል::ውስጥ ውስጡን እየቀሰቀሱ ችግር በፓርቲው ላይ የሚፈጥሩ ካድሬዎችን በማስወገድ በአዳዲስ ለመተካት ታቅዷል::

Image

ምንሊክ ሳልሳዊ ፦ ሰማያዊ ፓርቲ የጀመረውን ሰላማዊ ትግለ ለማጎልበትና የፓረቲውን መዋቅር የስራ እንቅሰቃሴ ለመገምገምና ለማጠናከር እነዲሁም መዋቅሩ ያለበትን ችግር መፍትሄ ለመስጠት ታስቦ የተዘጋጀ የመስክ ጉብኝት እንዲያደርጉ በሶስት ቡድን የተከፈለ ልኡካን በሃገሪቱ ማሰማራቱ ይታወቃል:: እነዚህ የልኡካን ቡድን አባላት የመስክ ጉበኝት በአጠቃላይ በ14 ዞኖችን የሚያካትት ሲሆን ወደ 200 የሚጠጉ ወረዳዎች ላይ ያሉ የሰማያዊን የፓርቲ እንቅስቃሴ ከሚመሩ አስተባባሪዎች ጋር ውይይት እያደረጉ በተግባራዊ ስራ ላይ ይገኛሉ::

በዚህም መሰረት በሚከተለው የመስክ ጉብኝት ምደባ መሰረት በሃገሪት የተለያዩ መስመሮች የተጓዙ የሰማያዊ ፓርቲ የመስክ ጉብኝት የሚያደርጉ አመራሮች …
ጉዞ መስመር አንድ ፡- ደ/ብርሀን ፤ ሸዋሮቢት ፤ ደሴ ፤ ወልዲያ
1. አቶ ስለሺ ፈይሳ – ም/ሊቀመንበርና የምርጫ ጉዳይ ኃላፊ
2. አቶ ዮናታን ተሰፋዬ – የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ
3. አቶ ሔኖክ መለሰ – በአደረጃጀት ጉዳይ የጥናትና የትግል ስልት ስልጠና ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ
ሸዋ ሮቢት ጨምሮ በደሴ መስመር ላይ ያሉ የሰሜን ሸዋ የፓርቲው የዞን/የቀጠና አመራሮችን በማወያየት ጉዞውን ወደ ወልዲያ እና ደሴ ያቀና ሲሆን ……

ጉዞ መስመር ሁለት – ደብረማርቆስ ፤ ባህርዳር ፤ ወረታ ፤ ጎንደር
1. አቶ በቃሉ አዳነ – አደረጃጀት ጉዳይ ም/ኃላፊ
2. አቶ ይድነቃቸው ከበደ – የህግ ጉዳይ ኃላፊ
3. ወ/ሮ ሃና ዋለልኝ የሴቶች ጉዳይ ኃላፊ የያዘ የጉዞ መስመር 2 ልዑክ ቡድን የካቲት 24 እና 25 ቀን 2006 ዓ.ም ከምስራቅ ጎጃም የዞን አስተባባሪዎች ጋር በደብር ማርቆስ ከተማ ውይይት አካሄደ፡፡
በምስራቅ ጎጃም ዞን 18 (አስራ ስምንት) ወረዳዎች የሚገኝ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ በ10 (አስሩ) ወረዳዎች ማለትም፡-
1ኛ. አነደድ 2ኛ. ደ/ማርቆስ ከተማ ወረዳ 3ኛ. ጎዛአምን 4ኛ. ማቻከል 5ኛ. ደብረ ኤሊያስ 6ኛ.ባሶ ሊበን
7ኛ. እናርጅ እናውጋ 8ኛ. ጎንቻ ሲሶእነሴ 9ኛ. እነብሴ ሳርምድርጉዞ መስመር ሁለት – ደብረማርቆስ ፤ ባህርዳር ፤ ወረታ ፤ ጎንደር/መርጦ ለማርያም 10ኛ. ሁለት እጁ እነሴ
ከላይ በተገለፁት ወረዳዎች የሰማያዊ ፓርቲ መዋቅር ተዘርግቶ ስራዎች እየተሩ ሲሆን ወደቦታው ያቀናው የልዑክ ቡድን እነዚህን ወረዳዎች ከሚያስተባብረው የዞን አስተባባሪ ኮሚቴ ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
በቀጣይ ቀናት በባህር ዳር፣ ወረታ (ደቡብ ጐንደር) እና ጐንደር በተመሳሳይ ሁኔታ የሰሜን ኢትዮጵያ ልዕካን ቡድን የሚንቀሳቀስባቸው ቦታዎች ናቸው፡፡

ጉዞ መስመር ሶስት – ሆሳዕና ፤ ሶዶ ፤ አርባ ምንጭ ፤ ባድዋቾ ፤ አዋሳ
1. አቶ ጌታነህ ባልቻ – የአደረጃጀት ጉዳይ ኃላፊ
2. አቶ ብርሃኑ ተ/ያሬድ – የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ
3. አቶ ይሁን ዓለሙ – የአደረጃጀት ጉዳይ የክትትልና ግምገማ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ የያዘው የመስክ ጉብኝት ቡድን ሶዶ ላይ ካለው መዋቅር ጋር አሰፈለጊውን ስብሰባና ግምገማ ካካሄዱ ቦሀላ ወደ ቀጣይ ከተማ ወደሆነችው አርባ ምንጭ ጉዞ ሲጀምሩ በሰዶ ፖሊሶች ተይዘው በአሁኑ ሰአት በእስር ላይ ይገኛሉ::

ከማንኛውም ሰው ጋር እንዳይገናኙ እና ምግብ እንዳይትገባላቸው የተደረጉት የመስክ ጉብኝት ቡድን ሶስት አባላት የመንግስታዊ ሽብር አሜኬላዎች የሆኑ ያልተማሩ ካድረዎች በበላይ ትእዛዝ በሚል ህገመንግስቱን በረገጠ መልኩ ሰላማዊ ትግልን መርጦ በመንግስት ተመዝግቦ በሚገኝ ፓርቲ እና አመራሮች ላይ የእስር እርምጃ መውሰዳቸው የዲሞክራሲ እሾዎች ማበባቸውን ያመለክታል:: ምንሊክ ሳልሳዊ

ምንሊክ ሳልሳዊ :- ኢትዮጵያ በታሪኳ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የመብቶች ሕጋዊነት በተጨበጨበለት ሁኔታ እና ይህ በማይባል ደረጃ በወረቀት ላይ ብቻ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ለይስሙላ እና ለማስመሰል የተደነገጉባት አገር ነች፡፡ የቀድሞ መንግስትን ሽንፈት ተከትሎ በኢትዮጵያ የሰብኣዊ መብት ጥሰቶች የፍፃሜ ምዕራፍ ይሆናል ተብሎ ተስፋ ተደርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ጭራሽ ብሶበት ቁጭ አለ፡፡ የሕወሓት ወንበሩን መቆጣጠር ተንተርሶ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በተለይም ሒዩማን ራይት ዎችና አምነስቲ ኢንተርናሽናል የወያኔን ጁንታ በሰብዓዊ መብት ጥሰት በማብጠልጠል ነበር የተቀበሉት፡፡ ባለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት የሰብኣዊ መብት ጥያቄዎች አቤቱታ ማሰማታቸውን አላቆሙም፡፡ ጋዜጠኞችን የሃሳብ ነጻነት ከሚገድብ ጥቃት በመከላከል ላይ የተሰማሩ የመብት አስከባሪ ድርጅቶችም ወያኔ በሚፈጥረው ከባድ የሰብኣዊ መብት ጥሰት በየጊዜው መክሰስ ሥራቸው ሆኗል:: የአሜሪካው ስቴት ዲፓርትመንት በየጊዜው በሚያወጣው ዓመታዊ መግለጫው ወያኔን በሰብዓዊ መብት ጥሰትና የፖለቲካ መብቶችን ማፈን ይከሰዋል፡፡ ባሁን ወቅት የእነኚህን አካላት መግለጫዎች የታወቁ ዓለም አቀፍ መገናኛ ድርጅቶች በመቀባበል ኢትዮጵያ የዜጎቿን መብቶች በመጣስና በማፈን ወደር የሌላት አገር እንደሆነች ዓለም እንዲረዳው እያደረጉ ናቸው፡፡

ታዋቂነታችን በድርቅ በድህነት ብሎም በጭፍጨፋ ደሞ በሰብኣዊ መብት ጥሰት የሕወሓት መራሹ ጁንታ ወደ ስልጣን በጠበንጃ ሃይል ከመጣ ጀምሮ በአለም አቀፍ ደረጃ የተደነገጉ የሰብአዊ መብት ህጎችን ካለምንም ማርቅርቅ እና ድካም ከሌሎች በመገልበጥ በወረቀት ላይ ከማስፈሩም በተጨማሪ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት በአለም ላይ የሰው አገር ህግን እና አለማቀፍ ድንጋጌን ከሃገራችን ሁኔታ ጋር ሳይገናዘቡ በስፋት በደመነፍስ ለፍጆታ የተጻፈበት ሃገር ኢትዮጵያ ብቻ ሲሆን በየትኛውም አለም ሃገራት ያልተከሰተ የአለም አቀፍ ህጎችን ግልባጭ በከፊል በህገመንግስት እንዲሁም የገዢ ፓርቲን የፖለቲካ ፕሮግራም በከፊል ደባልቆ በጋራ እንደ አውራ ህግ የወጣባት ሃገር ብትኖር ኢትዮጵያ ብቻ ናት::ኢትዮጵያ በታሪኳ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የመብቶች ሕጋዊነት በተጨበጨበለት ሁኔታ እና ይህ በማይባል ደረጃ የተደነገጉባት አገር ነች፡፡ እንግዲህ ይህ ሆኖ እያለ ነው በአገሪቱ የመብቶች ጥሰት ጉዳይ ከአገሪቱ ብሔራዊ አነታራኪ ፖለቲካዊ አጀንዳነት አልፎ ዓለም አቀፍ አጀንዳ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ጥላቻ በፈጠረው ፍርሃት ብቻ የሃገሪቱን ህጎች ዜጎች ለመጥለፍ እያዋሉት ነው::

ኢትዮጵያ በአስከፊ ድርቅና ረሃብ ለመታወቅ እንደበቃችው ሁሉ ወያኔ የዜጎችን መብቶች በመጣስና በማፈን እንዲሁም በሰብዓዊነት ላይ በሚፈጽመው ወንጀል በዓለም ላይ ታዋቂነትን እያተረፈ ነው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም;ወያኔ የፖለቲካ ተቀናቃኞችን መብቶች ለመጣስ ስለሚጠቀምባቸው ዘደዎች የሚቀርቡ ማስረጃዎች እና ማብራሪዎች እጅግ ዘግናኝ ናቸው፡፡የወያኔ መሪዎች የፖለቲካ ተቀናቃኖችን ለማዳከም ሲሉ ንፁኃንን ወንጀለኛ የሚያደርግ ዘዴዎችን ሥራ ላይ እንደሚያውሉ በተለያዩ ይፋዊ ሪፖርቶች ላይ ሁሉ ከነማስረጃው እየተነገረ ይገኛል::

ይህ የሰብኣዊ መብጥ ጥሰት እየተባባሰ የሚሄድበት ምክንያት ወያኔ በአብዛኛው ካድሬዎች ዘንድ በስፋት ሰርጾ እንዲገባ ያደረገው የተቃዋሚዎች ጥላቻ እና እንዲሁም የተቃዋሚው ቡድን የትግል አቅጣጫው በተመሳሳይ መልኩ በጥላቻ ላይ የተመረኮዘ መሆኑ ነው::ተቃዋሚዎች የታጠቁ ሃይላት ባለመሆናቸው የመርሃቸው እንቅስቃሴ የተገደበ እና ለፖለቲካ እና ለሚዲያ ፍጆታ የዋለ ተዳፍኖ የሚገኝ ሲሆን የወያኔው ግን በታጠቁ የጸጥታ ሃይሎች እና በፖለቲካ ማጭበርበሮች ላይ ስለተመረኮዘ ካድሬዎቹ በተሰጣቸው የጥላቻ ተግዳሮት እና ወያኔያዊ ስልቶች የፈጠሩትን ጥቅማጥቅሞች ጠብቀው ለማቆየት ሲባል ጥላቻ በፈጠረው ፍርሃት ብቻ የሃገሪቱን ህጎች ዜጎች ለመጥለፍ እያዋሉት ነው::

ይህ ፍርሃት እና ጥላቻ በወያኔ ከትልቅ እስከ ትንሽ ካድሬዎች አናት ውስጥ ስር ለስር በመስደድ የፈጠረው ነገር ቢኖር ማንኛውም ዜጋ ተቃውሞ ካሰማ በወንጀለኛነት በመፈረጅ በማሳደድ በማጥፋት እረፍት ለማግኘት እና ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ሲራወጡ የህዝብን የበላይነት አፈር ከተውታል::ማእከላዊ የወያኔ ጁንታ በዲሞክራሲ ባለመወቀጣቸው የህጎችን የበላይነት ማረጋገጥ ካለመቻሉም በተጨማሪ በህዝብ እና በዲሞክራሲ ላይ በደሎችን የሚያደርሱ ባለስልጣናት የሚጠየቁት በሃገሪቱ የበላይ ህጎች ሳይሆን በወያኔያዊ የፓርቲ መመሪያዎች በመሆኑ በጥቅም መተሳሰር በፈጠርው ዝግ መንገድ የሰብኣዊ መብት ጥሰቶች እየተብራከቱም ከመሆኑ አልፎ የእለት ተእለት ተግባራት አካል ሆነዋል::ምንሊክ ሳልሳዊ

“በሙስና በእምነት ማጉደል በማታለልና በአመለካከት የሚለዩን ዝም በማሰኘት ሐይልን የያዛችሁ በተሳሳተ የታሪክ ገጽታ ላይ ነው ያላችሁት! ቡጢያቹን የምትፈቱ ከሆነ እጅ እንዘረጋላችሗለን” ያሉት ኦባማ አንባገነናዊ ቡጢያቸዉን ካልፈቱ…አንባገነናዉያን ጋር እጃቸዉን ዘርግተዉ ሲጨባበጡ መታየታቸዉ ትዝብት ላይ እየጣላቸዉ ነዉ!

ዋሽንግተን ዲሲ፤ የካቲት 24/2006 (ቢቢኤን) ፦ የዩናይትድ እስቴትስ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉን ገደብየለሽ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ለማመላከት ያደረጋቸዉን ጥናቶች ዋቢ በማድረግ በየካቲት 20/2006 ሪፖርቱን ይፋ አድርጓል።መሰረቱን አርሊንግተን ቨርጂኒያ ያደረገዉ ፖለቲኮ የሚባለዉ ጋዜጣ/መጽሔት የኦባማ አስተዳደር የኢትዮጵያ መንግስትን ከመሰሉ ለነጻነት ምቹ ካልሆኑ አገራት ጋር ያለዉ ምጸታዊ የዲፕሎማሲ ቁርኝትንም ይተቻል።

ከቀዝቃዛዉ ጦርነት ጀምሮ የዩናይትድ እስቴትስ መንግስታት ዜጎቻቸዉን ከሚጨቁኑ አገራት ጋር ግንኙነት ለመመስረት እምብዛም እንደማይጥሩ ፖለቲኮ እየገለጸ፤ለሚዛናዊነቱ ተስፋ የተጣለበት የኦባማ ካቢኔ ከሌሎቹ የዩናይትድ እስቴትስ ፕሬዝዳንቶች በባሰ መልኩ ለዜጎቻቸዉ ደህነነት ምቹ ካልሆኑ 25 አገራት ጋር ግንኙነት አለዉ ሲል የኦባማን የብሐራዊ ደህነነትና ጥበቃ አማካሪ የሆኑትን ሱዛን ራይስ ንግግርን በዋቢነት ያቀርባል። ራይስ “ግልፅ እንሁን አንዳንዴ እኛ አጥብቀን የምንይዛቸዉን ዉድ የሆኑ መብቶችን ከማያከብሩ መንግስታት ጋር የስራ ግንኙነት አለን” በማለት በባለፈዉ የነሐሴ ወር መናገራቸዉን ፖለቲኮ ይገልጻል።

ፖለቲኮ ለነጻነት የማይመቹ ብሎ ከጠራቸዉ 25 አገራት ዉስጥ ኢትዮጵያን በቁጥር 11 ላይ ያስቀመጠ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስቴር ሐይለማሪያም ደሳለኝ ይመሯታል የምትባለዋ ኢትዮጵያ የጸረ-ሽብር ህጓን ፖለቲከኞችን፣አክቲቪስቶችን፣መንግስትን ተጠያቂ የሚያደርጉ አካላትን ለማሰር እንደ ማህተም ትጠቀምበታለች ሲል ተጠያቂ ያደርጋል።ፖለቲኮ አክሎም የመለስ ዜናዊ አስተዳደር በ1999 ሶማሊያን በመዉረር እራሱን ለዩናይትድ እስቴትስ ግልጋሎት ማቅረቡንያስረዳል። ይህንንኑ አጋጣሚ በመጠቀም በአሜሪካ የሰለጠኑ የኢትዮጵያ ወታደሮች ከብሔር ብሔረሰቦች የተነሱ አማጺያንን ለማስቆም የጦርነት ወንጀል መፈጸማቸዉ በሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ክስ ቢቀርብበትም ዋሽንግተን አዲስ አበባን በዲፕሎማሲ “እቅፍ-እቅፍቅፍ” እያደረገች መቀጠሏን ገልጿል።

ኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብትን ይጥሳሉ ከሚባሉት ጭቋኝ አገራት ጎራ ብትመደብም ፤እንደ አዉሮፒኣይኑ ቀመር በ2008 ብቻ ከዩናይትድ እስቴትስ 969 ሚሊዮን ዶላር በእርዳታ ተቀብላለች!

በኢትዮጵያ ዉስጥ ቀጣይ የሆነ የሰብዓዊ መብት ረገጣ፣ግድያ፣እስር፣የሐይማኖትነጻነትን መነፈግ፣የፕሬስ ነጻነት መመንመን፣የመማርና ማስተማር ሒደት ነጻነት በመንግስት መዳፍ ዉስጥ መግባት፣የመደራጀት-የመሰባሰብ-ሐሳብን በነጻ የመግለጽ ሁለንተናዊ መብት፣ የፍርድ ቤት አሰራር መበላሽትና በስልጣን መባለግን በመተንተን የዩናይትድ እስቴትስ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በየካቲት 20/2006 አመታዊ ሪፖርቱን ይፋ አድርጓል። የኦባማ አስተዳደር አካል የሆነዉ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አሳቃቂ የሆነ የመብት ረገጣ ኢትዮጵያ ዉስጥ መኖሩን እያወጀ የኦባማዉ ቤተ-መንግስት ኢትዮጵያን ከመሰሉ በአንባገነናዉያን ከሚመሩ አገራት ጋር “መለስ-ቀለስ” ማለቱ እያስተቸዉ ነው። የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱን የሚመሩት ጃን ኬሪ አገራቸዉ ከስህተት የጠራች አለመሆኗን ያስረዳሉ።

“ዛሬ ስለ ሌሎች አገራት ያለዉ ሪፖርት ይፋ ለማድረግ ብንመጣም፤ እዚሁ አገራችን ላይ እራሳችንን በከፍተኛ መልኩ ተጠያቂ እናደርጋለን! እንከን የለሽ አለመሆናችንን እናዉቃለን” ጃን ኬሪ።

ጃን ኬሪ መስሪያቤታቸዉ ይፋ ያደረገዉ የሰብዓዊ መብት ሪፖርት ዋሽንግተን ዲሲ ባሉ የመስሪያ ቤቱ አባላት ጥናት ብቻ የተዘጋጀ ሳይሆን በእያንዱ አገራት ያሉ ኤምባሲዎችና ቆንስላ ጽ/ቤቶች ተሳታፊ መሆናቸውን ሲያስረዱ “በመላዉ አለም ያሉ ኤምባሲዎችና ቆንስላ ጽ/ቤቶች በጥናት እንደዚሁም እነዚህን ጽሁፎችን በመጻፍ አክቲቪስቶችን በመቅረብ መንግስታትን በማናገር የኤንጂኦና የሚዲያ ሪፖርቶችን በመተንተን አያሌ ሰአታትን አባክነዋል”ሲሉም ገልጸዋል።

ኬሪ ለነጻነትና ለመብት በሚደረግ ጥረት ዉስጥ ግለሰባዊ ሚና የጎላ መሆኑን መሆኑንም ይገልፃሉ።ከተለያዩ አገራት የለዉጥ ተምሳሊት የሚሏቸዉን ግለሰቦችን ስም በማንሳት የኢትዮጲያዉን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ሚናን አድንቀዋል “እስክንድር ነጋ ሐሳብን በነጻ ስለመግለጽ ኢትዮጵያ ዉስጥ የሚጽፍ ነው” ብለዋል።

በሚያዚያ 4/2004 የፔን አሜሪካን ሽልማትን ያገኘዉ እስክንድር ነጋ አለም አቀፋዊ ትኩረትን ያገኘ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ ነዉ። የኢትዮጵያ መንግስት በሽብር ፈጠራ ወንጅሎት ከመስከረም 3/2003 ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛል።

የዩናይትድ እስቴስ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ነጻነትን ከሚነጥቁ ጥቂቶች ጋር ሳይሆን ነጻነትን ከተነፈጉ ብዙሗን አጋር በመሆን አብሮ እንደሚቆም ኬሪ ቃላቸዉን እያደሱ ይናገራሉ “ዛሬ ቃላችንን በድጋሚ ለማረጋገጥ እንወዳለን! ክብርን ከሚነፍጉ ጥቂቶች ጋር ሳይሆን ክብርን ከሚሹ ብዙሗን ጋር አብረን ለመቆም ዝግጁ መሆናችንንም ለመግለጽ እንወዳለን!”በማለት ቢያስረዱም መንግስታቸዉ ከጨቋኝ አንባገነናዊያን ጋር በሚያደርገዉ ዲፕሎማሲያዊ ቅርርብ ተጠያቂ እየሆነ ነው።

በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ብዙ ቃልኪዳን የገቡት በራክ ኦባማ ቃሊኪዳናቸዉ አለተፈጸመም። በተመሳሳይ መልኩ ያሁኑ የዉጭ ጉዳይ መስራያ ቤት ሐላፊ ጃን ኬሪም ሆኑ የቀድሞዋ ሒላሪ ክሊንተን ከአንባገነናዊያን ጋር ያለዉን ግንኙነት ሲያደረጁ እንጂ ሲያመነምኑ አልተስተዋለም በማለት በርካታ ምሁራን፣ጋዜጠኞች እና የፖለቲካ ተንታኞች ወቀሳ ያቀርቡባቸዋል።

በጥር 12/2001 ቃለመሃላ የፈጸሙት ፕሬዝዳንት ኦባማ ሰላምና ክብርን ለሚሹ የአለማችን ዜጎች የርሳቸዉ መመረጥ ብስራት እንደሆነ አመላክተዉ ነበር። ከትላላቅ የአለማችን መዲናዎች ጀምሮ ወላጅ አባታቸዉ እስከመጡበት የኬኒያ መንደር የተስፋ ቃል ነበራቸዉ! እንዲም በማለት ስሜትን በሚነካ መልኩ ተናግረዉ ነበር…

“ከትላልቆቹ መዲናዎች እስከ አባቴ የተወለደባት መንደር ዛሬ ለሚመለከቱን ህዝቦችና መንግስታት፤ አሁን አሜሪካ የእያንዳንዱ አገር የእያንዳንዱ ግለሰብ ወዳጅ ናት! ሰላምና ክብርን ለሚፈልጉ ሴቶችና ህጻናት ዳግም ለመምራት ዝግጁ ነን” ፕሬዝዳንት በራክ ኦባማ።
ኦባማ ምንጫቸዉ ለሆነችዋ አፍሪካ ፕሬዝዳንታዊ ሐይላቸዉን በመጠቅም ያበረከቱት አስተዋፅኦ አናሳ ነዉ።ፕሬዝዳንቱ ቃለመሃላቸዉን ሲፈጽሙ ስልጣንን በማጭበርበር-በሙስናና የሐሳብ ልዩነትን በማፈን በሚቆናጠጡ አንባገነናዉያን ላይ ጣታቸዉን ቢቀስሩም ከነዚህ ምቹ ያልሆኑ አሳፍሪ መንግስታት ጋር እርሳቸዉም ይሁን ካቢኔአቸዉ ዲፕሎማሲያዊ ገደብን አለማበጀቱ አጠያያቂ እየሆነ ነዉ።

በአሜሪካዋ መዲና በዋሽንግተን ዲሲ ጥር 12/ 2001 ቀዝቃዉ አየር በጭብጨባ እየሞቀ ብዙዎች እያለቀሱ ኦባማ ለአንባገነናዊያን መልእክት አስተላልፈዋል…

“በሙስና በእምነት ማጉደል በማታለልና በአመለካከት የሚለዩን ዝም በማሰኘት ሐይልን የያዛችሁ በተሳሳተ የታሪክ ገጽታ ላይ ነው ያላችሁት! ቡጢያቹን የምትፈቱ ከሆነ እጅ እንዘረጋላችሗለን” ያሉት ኦባማ አንባገነናዊ ቡጢያቸዉን ካልፈቱ…አንባገነናዉያን ጋር
እጃቸዉን ዘርግተዉ ሲጨባበጡ መታየታቸዉ ትዝብት ላይ እየጣላቸዉ ነዉ።

ብዙ የተገቡ ቃልኪዳስኖች ተግባራዊ ሳይሆኑ በየካቲት 20/2006 ከዩናይትድ እስቴትስ የዉጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የአመቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲታወጅ “ከነጻነት ፈላጊዎች ጋር እንቆማለን!” የሚል ቃልኪዳን ተገብቷል።የዩናይትድ እስቴትስ መንግስት ባወጣዉ የሰብዓዊ መብት ሪፖርት የኢትዮጵያን መንግስት “ጨቋኝ-አፋኝ-አሳሪ-ገዳይ-ኢዲሞክራሲያዊ” መሆኑን ይፋ አድርጓል። ፖለቲኮ ጋዜጣ/መጽሔት ይህ ሪፖርት በወጣበት ማግስት የኦባማ አስተዳደር ኢትዮጵያን ከመሰሉ ለዜጎቻቸዉ ምቹ ካልሆኑ አገራት ጋር ይወዳጃል ሲል ይተቻል።

የዲሞክራሲ ተምሳሊት ነን የሚሉ የምእራቡ አገራት ለአንባገነናዊያን ዲፖሎማሲያዊ ከለላ መስጠታቸው የጥቅም ትስስር ወይስ ምጸታዊ የሆነ የዲፕሎማሲ ጨወታ? የሚለዉ ጥያቄ ቢነሳም …ትችቱእንደቀጠለ ነዉ።

ሳዲቅ አህመድ

የደሴ ሕዝብ ከመለስ ፋውንዴሽን ጋር በተያያዘ ከአምስት ሚሊዮን ብር በላይ ይፈለግበታል::

ምንሊክ ሳልሳዊ :- ከደሴ የሚደርሱኝ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት በሕወሓት አዛዥነት በብኣዴን ሰብሳቢነት የመለስ ዜናዊን አመራር አካዳሚ ሕንጻን ለመገንባት የመለስ ፋውንዴሽን ከህዝቡ ከአምስት ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚጠበቅበት እና ለግንባታው የግዴታ አስታውጾ እንዲያደርግ እያስገደዱት መሆኑን እና ሕዝቡም ከኑሮ ውድነት ጎን ለጎን ከአፉ ላይ ሊጎርሰውን ያዘጋጀውን በጉልበተኞች እየተነጠቀ መሆኑን በማማረር አቤቱታውን ማሰማቱን የደሴ የለውጥ ሃዋርያ ወጣቶች አንድነት ለምንሊክ ሳልሳዊ በላከው መረጃ ገልጽዋል::

መረጃዎቹ እንደጠቆሙት የገንዘብ አሰባሰቡ ሂደት በሁሉም ክፍለከተሞች ባሉ የወያኔ ካቢኔዎች ሲሆን እያንዳንዱ የካቢኔ አባል በግል እንዲሰበስብ የገንዘብ መሰብሰቢያ ደረሰኝ የተሰጠው ሲሆን ከፍተኛ ገንዘብ ለሰበሰበ ሽልማት ስለሚሰጠው የሚል ቅል ስለተገባላቸው የስልታን እና የደሞዝ እድገት ለማግኘት እና ታማኝነታቸውን ለማረጋገጥ በሽፍን ድጋፍ ሕዝቡን በግዳጅ እና በማስፈራራት በዛቻ ገንዘብ እንዲያዋጣ እያደረጉት ሲሆን ይህንን በተመለከተ ሕዝቡ በቤቱ አሊያም በስብሰባ ካልተገኘ በቅጣት ሁሉ መልክ ተጨማሪ እንዲከፍል ይደረጋል የሉት የምንሊክ ሳልሳዊ ምንጮች ሕዝቡ በሚሄድበት መስሪያቤት አሊያም ስብሰባ ቀደም ብሎ የከፈለ ሰው ደረሰኙን ካልያዘ ጉዳዩን ለማስፈጸም በድጋሚ እንዲከፍል የሚደረግ ሲሆን እረስቸዋለሁ ሄጄ ላምጣ የሚል ነገር ተቀባይነት የለውም::

እንዲሁም በደሴ የብኣዴን ጽ/ቤት ሃላፊነት ተጨማሪ ለመለስ ፋውንዴሽን በሚል በግዳጅ ገንዘብ እየተሰበሰበ ሲሆን የጽ/ቤቱ ሃላፊ የሆኑት አቶ ጌታዊ ይርጋ (የቀድሞ የኮምቦልቻ ከተማ ከንቲባ) ከዚህ ቀደም በሙስና ታስረው የነበሩ እና ከህግ ውጪ ለፖለቲካው አስፈላጊ ሆነው በመገኘታቸው በትእዛዝ ከተፈቱ በኋላ ሲቭል ሰርቭስ ኮሌጅ ተልከው ሰልጥነው በደሴ የብኣዲን ጽ/ቤት ሃላፊ ሆነው ከተመደቡ ጀምሮ በግዳጅ ከእጅ ወደ አፍ የሚኖረውን በኑሮ ውድነት የተማረረውን ህዝብ እያስገደዱ የመንግስት ሰራተኛውን ከደሞዙ ላይ 30% እንዲቆረጥ ውሳኔ በመስጠት እንዲሁም በየቤቱ የብኣዴን ካድሬዎች እየዞሩ ከቀበሌ ሰዎች ጋር በመሆን ሕዝቡ 100 ብር እንዲከፍል በበደል ላይ በደል እየፈጸሙበት ይገኛል:: እንዲሁም ባለሃብቱን እያስገደዱት ያሌለን ገንዘብ እንዲተፋ ወጥረው ይዘውታል ሲሉ ለምንሊክ ሳልሳዊ መረጃውን ልከዋል::
=================ምንሊክ ሳልሳዊ====================
በሌላ ዜና በደዜ ከተማ ዙሪያ ጨለማን ተገን አድርገው የሰዎች ግድያ እና ዝርፊያ ወንጀሎች ከበፊቱ በበለጠ በመበርከቱ የከተማው ፖሊስ መምሪያ ማንኛውም የከተማው ነዋሪ ከምሽቱ አራት ሰአት በኋላ ምንም አይነት እንቅስቃሴ እንዳያደርግ የሰአት እላፊ ገደብ መጣሉን የከተማው ነዋሪዎች ለምንሊክ ሳልሳዊ በስልክ ገልጸውለታል::

ባለፉት ሁለት ቀናት በመላው አገሪቱ የተካሄዱትን ፍተሻዎች በተመሳሰለ መልኩ የሞባይል ቤቶች እና የኢንተርኔት ካፌዎችን እንዲሁም የመረጣቸውን ብሎም የጠረጠራቸውን ግለሰቦች በድንገት ፍተሻ በማካሄድ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሞባይሎች ላፕቶፖች ዲስክቶፖች ኮምፒተሮች እና የሚሞሪ ካርዶች ሰብስቦ የወሰደው የደሴ ፖሊስ ሰአት እላፊውን ጥሶ የተገኘ ነዋሪ በጸጥታ ሃይሎች ለሚወሰድበት ማንኛውም እርምጃ መንግስት ተጠያቂ እንደማይሆን ገልጿል::

ከዚሁ ጋር በተያያዘ መረጃ የደሴ ከተማ በፌዴራል ፖሊስ ወታደራዊ ልምምድ ተወጥራ እንደምታመሽ ታውቋል:; ቁጥራቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ የፌዴራል ፖሊሶች ከምሽቱ 3 30 ጀምሮ ወታደራዊ ልምምድ ለማድረግ በዋናው የከተማዋ መንገዶች በመጠቀም ላይ ሲሆኑ በህዝቡ ላይ ሽብር እየነዙ መሆኑን ምንጮቹ ለምንሊክ ሳልሳዊ ነግረውታል::ይህንን እያደረጉ ያሉት የከተማውን ነዋሪ ለማስፈራራት እና ለማሸበር እየጣሩ እና በሃርቡ አከባቢ የሚንቀሳቀሱ የፌዴራል ፖሊሶች ለሊቱን በወታደራዊ ልምምድቸው ጊዜ ስለሚጮሁ ህዝቡን ከስራ ቤቱ ገብቶ እንዳያርፍ እንቅልፍ እየነሱት ሲሆን ምን ያክል መንግስት ጭንቀት ላይ እንዳለ ያሳያል ሲሉ መረጃውን የላኩት ነዋሪዎች ገልጸዋል::መረጃውን ላቀበላችሁኝ የደሴ ወጣቶች አመሰግናለሁ ምንሊክ ሳልሳዊ::

Image

ውህደት ለምን ይኮነናል? በዳንኤል ተፈራ
#Ethiopia #UDJ #AEUP #Blueparty #EPRDF #Ginbot7

ሰሞኑን በውህደት እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ዘመቻ ተከፍቷል፡፡ እየተለፋበት ባለው የውህደት እንቅስቃሴ ላይ ዘመቻ የከፈቱ ኃይሎችን በሦስት ከፍሎ ማየት የሚቻል ይመስለኛል፡፡

1ኛ. ኢህአዴግ ሲሆን ተቃዋሚዎችን በተበታተነ ሁኔታ በመግጠም አሸናፊ ሆኖ መውጣት ይቻላል ብሎ ስለሚያምን ነው፡፡ ወደ ኮሮጆ ግልበጣ ከሚሄድ ይልቅ ተቃዋሚዎችን ከፋፍሎ ወይም ተሰባስበው አንድ ትልቅ የፖለቲካ ሃይል እንዳይፈጥሩ በማድረግ ለማሸነፍ መሞከር የመጀመሪያ ምርጫው ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ውህደቶች እንዳይሳኩ ትግል ማድረጉን ይቀጥላል፡፡ በአጠቃላይ ዉህደት ለዚህ ስርዓት አይመቸውም፡፡

2ኛ. በሁለተኛነት ብቻችንን የኢትዮጵያን ፖለቲካ መሸከም እንችላለን የሚሉ ወገኖች እንዲሁ የውህደት እንቅስቃሴው ላይ ቀስት ለመስበቅ የተጣደፉ ይመስለኛል፡፡ ባለብዙ መልኩ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ግን ለእንደዚህ አይነት ሀሳብ የሚመች አይደለም፡፡ ፖለቲካችን ወደድንም ጠላንም አታካችም ቢሆን የተለያዩ አስተሳሰቦችን ማቀራረብ የሚፈልግ፣ በውይይት መለዘብ የሚገባውና በብሄርና ህብረብሄር ጫፎች የተወጠረ ነው፡፡ ስለዚህ በሀገር ጉዳይ ላይ መወያየትና ውህደት መፍጠር ተገቢ ነው፡፡ አንድን ‹‹ግሩፕ›› ብቻ እወክላለሁ የሚል የፖለቲካ ሃይል ውህደትን በመኮነን፣ ያውም ውህደት ያስፈልጋል የሚሉ የፖለቲካ ሃይሎችን ሀሳብ ሳያከብርና በጣም ተራ የሆነ ምክንያት እየሰጠ ውህደቱ እንዳይሳካ ይታገላል፡፡ ቢያንስ ብቻየን የኢትዮጵያን ፖለቲካ እሸከማለሁ ማለት መብት እንደሆነ ሁሉ ውህደት ያስፈልጋል ማለትም መብት እንደሆነ የሚያምን አይመስለኝም፡፡ እናም ወንጋራ ሀሳብ የሚያቀርቡ አንዳንድ ግለሰቦች ቆም ብለው ቢያስቡ መልካም ይመስለኛል፡፡

3ኛ. በሦስተኛነት ውህደትን የሚኮንኑት በቅንነት የተቃውሞ ጎራው በመዋሃድ ትልቅ ሃይል መሆን ይገባዋል ብለው ሲወተውቱ የነበሩትና እስካሁን በውህደት ትልቅ ሃይል አለመፈጠሩ የሚያስቆጫቸው አንዳንድ ግለሰቦች ናቸው፡፡ ግን ደግሞ ፖለቲካ ያው ፖለቲካ ነውና እንደ ቅን ሰዎች ሃሳብ ነገሮች ላይሄዱ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ በሆደ ሰፊነት ውህደቶች እንዲሳኩ መጣር የእያንዳንዱ ሀገር ወዳድ ሁሉ ውትወታና ስራ መሆን አለበት፡፡ በመጨረሻ ግን እኔ በግሌ እንደማምነው የኢትዮጵያን ፖለቲካ የተወሰኑ ግለሰቦች ሊሸከሙት እንደማይችሉ ነው፡፡ ምናልባት ወደፊት ግን ይቻል ይሆናል፡፡ የግለሰቦች መብት የሚረጋገጥበት ስርዓት ከተዘረጋ በኋላ ማለት ነው፡፡ ጎበዝ አሁን እየተደረገ ያለው ትግል ግን ስርዓት የመፍጠር ነውና ሃሳብን እያቻቻሉ መዋሃድ ተገቢና ወቅታዊ ነው፡፡

የሃገራቸው ነገር ሲነሳ የሚከነክናቸው ወገኖቻችን ኢትዮጵያ ለባት ችግር መፍት ሄው ምንድነው? እያሉ ኣጥብቀው ሲጠይቁ ይደመጣል። መፍትሄውም ብቻ ሳይሆን ችግሩ ማለትም እውነተኛው ችግር የት ላይ ነው ያለው? ብለውም ኣጥብቀው ሲደመሙ ይታያል። በዛሬዋ ኣጭር ጽህፌ በነዚህ መራራ ጥያቄዎች ዙሪያ ቁንጥል ኣሳብ ለማቀበል ኣስቢያለሁ።

በርግጥም ሁላችን ኢትዮጵያዊያን የሆንን ችግሩ ምንድነው? ብለን ከጠየቅን ኣንዳንዶች ሊገረሙብን ይችላሉ። የችግሩ ተካፋይ ሆነን ሳለ፣ እየተጉላላን ያለነው እኛው ሆነን ሳለ፣ እንደገና መልሰን የሃገራችን ችግር የት ጋር ነው? ብለን ስንጠይቅ የምናወጋቸው ሰዎች ምናልባትም ግራ ሊጋቡ ቢችሉ ኣይደንቅም። ነገር ግን መጠየቃችን ትክክል ነው።

በመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ትንቢተ ዳንዔል ላይ ኣንድ ናቡከደነጾር የተባለ ንጉስ ኣንድ ጊዜ ጠቢባንን ጠርቶ የህልም ፍቺ ይጠይቃል። ጥበበኞቹም ህልሙን ንገረንና ፍቺውን እንነግርሃለን ሲሉት ህልሙ ጠፍቶብኛል ስለዚህ ህልሙንም ፍቺውንም ውለዱ ብሎ ጉድ እንዳፈላ እናነባለን። እኛ ኢትዮጵያዊያን የዋናው ችግር ተጽእኖዎች የየእለት ኑሮኣችንን ሲያምሱት ብናይም ዋናውን የችግሩን ምንጭ መፈለጋችን ግን ኣሁንም ትክክል ነው።

የሃገራችንን ዋና ችግር የት ጋር ነው ብለን ኣጥብቀን ከጠየቅን በርግጥ የስርዓት ችግር ነው ወይ? ስርዓት በማጣታችን ነው ወይ የከፋ ችግር ላይ የወደቅነው? ብለን እንጠይቃለን። በዚህ ኣገባብ ስርዓት ስንል የኣይዲዮሎጂውን ጉዳይ ሳይሆን ፍትህና ተጠያቂነት፣ ግልጽነትና የህዝብ የበላይነት የሚንሸራሸርበት ሲስተም ተዘርግቷል ወይ ብሎ የመጠየቅ ያህል ነው። ስለ ስርዓት ስናነሳ ደግሞ በዋናነት የሚታየው ህገ- መንግስታዊ ስርዓቱ ነው። ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱ ምን ያህል ለዜጎች ይጨነቃል፣ ምን ያህል ለፍትህና ለነጻነት ለህዝቦች ጥቅም መንሸራሸሪያ ይህናል? ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናል። በዚህ ረገድ በርግጥ መሻሻል ያለባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም በዋናነት ግን ችግራችን የስርዓት ችግር ሆኖ ኣናይም። ለኣብነት የ1955ቱን ህገ መንግስት ስናይ የፕሬስ ነጻነትን ይሰጣል፣ እኩል የህግ ከለላ ይሰጣል፣ የመሰብሰብ፣ ሰልፍ የማድረግ መብትን ሁሉ ይሰጣል። የደርጉም ቢሆን ለዜጎች የሚጨነቅ ኣይነት ነው። “ኢትዮጵያዊያን በህግ ፊት እኩል ናቸው” ይላል። ከሁሉ በላይ ደግሞ የ1995ቱን ስናይ “ሰብዓዊ መብቶችና ነጻነቶች ከሰው ልጅ ተፈጥሮ የሚመነጩ የማይጣሱና የማይገፈፉ ናቸው” ብሎ እጅግ ኣጠንክሮ ለዜጎች መብት መቆሙን ይደነግጋል። በውነቱ ይህ ኣንቀጽ ብቻውን ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ዋስትና ይሆን ነበር። ይሁን እንጂ ተግባራዊው እውነት ደግሞ ለብቻው በተቃራኒው ተንሰራፍቶ ይታያል። ይህ ለምን ሆነ? እንዴት እንዲህ ሊሖን ይችላል? ብለን ነው መጠየቅ ያለብን። እንዲህ ስንጠይቅ የችግሩ ዋና ጉዳይም የስርዓት እጦት ሳይሆን ሌላ ጉዳይ መሆኑን እንረዳለን። በርግጥ ለወደፊቱዋ ኢትዮጵያ የተሻለ ስርዓት ማምጣት ያስፈልጋል። በተለይም ብዙህነቱዋን ተንከባክቦ የሚይዝ ማህበራዊ የፖለቲካ ስርዓት ያሻናል። ያ ማለት ግን ከችግራችን እንድንወጣ ብቻውን ዋስትና ነው ማለት ኣይደለም። የቱንም ያህል ጥሩ ስርዓት ዘርግተን ከችግራችን ሳንወጣ ልንቆይ እንችላለን። ርግጥ ነው የማንነት ፖለቲካ ማህበራዊ ቀውስን ያመጣ ችግሮች የበለጠ እንዲነዱ የሚያደርግ ጉዳይ በመሆኑ ከዚህ መንግስት ውድቀት በሁዋላ ከዚህ የፖለቲካ መዋቅር መውጣታችን ለመፍትሄ ትልቅ በር ኣለው። ይሁን እንጂ ኣሁንም ቢሆን የቱንም ያህል ቆንጆ ስርዓት እናምጣ ኢትዮጵያን ከመከራና ከርሃብ የሚያወጣት እሱ ብቻውን ኣይደለም። ታዲያ ምንድነው? የሚል ጥያቄ መምጣት ኣለበት። ኣዎ፣ ዋናው የሃገራችን ችግር ያለው የፖለቲከኖች ስብእና ተክለሰውነት ወይም ፐርሰናሊቲ ጋር የተገናኘ ነው።

ሃገራችን ከችግር እንድትወጣ ከተፈለገ የፖለቲካ ቁርጠኝነትን ይጠይቃል። የችግሮቻችን ቁንጮም የፖለቲካ ቁርጠኝነት እጦት ነው ብሎ መደምደም ይቻላል።የፖለቲካ ቁርጠኝነት ስንል ኣንድ ፓርቲ ስልጣን ከያዘ በሁዋላ የፍርድ ቤቱን ልጓም ለቀን መልሶ ከበላንም ይብላን፣ በራሳችን ላይ ይፍረድብን፣ ብሎ በራስ ላይ የመወሰን ኣቋም ነው። ወታደሩን ኣገርህን ጠብቅ የፓርቲ ጠባቂ ኣይደለህም ኣንተ ኣገር ጠባቂ ነህ ለማለት የፖለቲካ ሰዎችን ቁርጠኝነት ይጠይቃል። ፖሊሱን፣ ባንኩን፣ ሚዲያውን ሁሉ ልጓሙን ለቆ በሙያህ ኣገልግል ብሎ መወሰን ሲቻል ነው ከገባንበት ኣረንቋ የምንወጣው። የናፈቀንን ዴሞክራሲ በህይወት የምናየው። ጥያቄው ይህ የፖለቲካ ቁርጠኝነት እንዴት ሊመጣ ይችላል ነው። የፖለቲካ ቁርጠኝነት ከጥቂት የፖለቲካ መሪዎች ከራስ ጥቅምና ዝና በላይ የህብረተሰብን ዝናና ጥቅም በተጠሙ ሰዎች ሊነቃነቅ ይችላል። ኣንድ ቁርጠኛ መሪ ኣገር ሊለውጥ ይችላል። በታሪክ የታዩ ኣንዳንድ ቁርጠኛ መሪዎች በየሃገሩ ተነስተው ጥሩ መሰረት እየጣሉ ኣልፈዋል። በሃገራችንም የተጠማነው ይህንን ነው።

በኣሁኑ ጊዜ ተቃዋሚው ክፍል መንግስትን ኣጥብቆ ማውገዙ ትክክል ነው። የህዝቡም ልብ ነጸብራቅ ነው። ይሁን እንጂ ይህ መንግስት በማንኛውም መንገድ ሲወድቅ ስልጣን ይዞ ጥሩ ስርዓት መዘርጋቱ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ቁርጠኝነት (political commitment) ያላቸውን ሰዎች ይዘዋል ወይ? ብለን እንድናስብ ያደርገናል። በዚህ ረገድ ተቃዋሚው ጥቃቅን በሆኑ ፖሊሲዎች ከመከፋፈል ይልቅ ወደ ጋራ እያመሩ ከሁሉ በላይ የፖለቲከኞችን ስብእና የመገንባቱ ላይ ማተኮር ለነገይቱ ኢትዮጵያ ዋስትና ይሆናል። ይህን ስብእና ወይም ተክለሰውነት የመገንባት ስራ ፓርቲዎችን ቢዚ የሚያደርግ ወቅታዊ ስራ መሆን ኣለበት። ኢትዮጵያ በኣሁኑ ደረጃዋ ጥቃቅን ፖሊሲዎችን በማነጻጸር የምታማርጥበት ጊዜ ላይ ኣይደለችም። መሰረታዊ የሆኑ ጉዳዮችን ያጣች በመሆኑዋ የስካንዲኒቪያው ኣይነት ዴሞክራሲ ይሻልሻል የኣሜሪካው ኣይነት? ማለቱ ያልበላትን የማከክ ያህል ነው። ሁሉቱም ሆኖላትስ ነው?
ዋናው በኣሁኑ የኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጉዳይ ፓርቲዎች እኔ እሻላለሁ ለማለት ዋናው መመዘኛቸው የተሰባሰቡት በተለይም ኣመራር ላይ ያሉት ግለሰቦች የፖለቲካ ቁጠኝነት ኣላቸው ወይ? ቁርጠኝነት በሞላቸው ሰዎች ቁጥር የትኛው ፓርቲ ያይላል? የሚል ልብ ያለው ድጋፍ ነው በተግባር የሚታየው ወይም መታየት ያለብት።

በቲየሪ ደረጃ በኣሁኑዋ ኢትዮጵያ በፍርድ ቤት ጉዳይ መንግስት ጣልቃ ኣይገባም። ይሁን እንጂ በተግባር ይገባል። ይገባል ብቻም ሳይሆን ፍርድ ቤት የፖለቲካ መሳሪያ ነው። ኣሁን እዚህ ጋር የጎዳን የስርዓቱ ወይም የኣሰራሩ ጉዳይ ሳይሆን መከራ ውስጥ የከተተን ጉዳይ የግለሰቦች ስብእና ጉዳይ ሆኖ ነው የምናየው። ለምን እነዚህ ግለሰቦች ስርዓቱን ይጥሳሉ፣ ህጉ ለምን ኣቅም ያጣል? ካልን የፖለቲከኞቹ ላእላይ ስብስብ በተለያየ የግል ጥቅማጥቅም የተተበተበ በመሆኑ ነው። ድህነታችንም ኣንዱ ኣስተዋጾ ያደረገ ይመስላል። የተሻለ ስራ ለማግኝነት፣ ከድህነት ለመላቀቅ፣ ፖለቲካን መሳሪያ ማድረጉ የተለመደ መሆኑና ወደዚያ ጠጋ ያሉ ሃላፊዎች በዚህ ሞቲቭ የተሞሉ ስለበዙበት ስርዓቱ በቁሙ እንዲሞት ኣድርጎታል።

ባለፈው ጊዜ ኢትዮጵያ ብሄራዊ እርቅ ኮሚሽን ማቋቋም ያስፈልጋታል የሚል ኣንድ ኣርቲክል ጽፌ ነበር። በርግጥም በኣሁኑ የነጻነት ትግል ኣሰላለፍ በኩል ጎድሎ የታየው ይሄ ነውና ይህንን ማቋቋም ተገቢ ነው። ይህ ኮሚሽን ፓርቲዎችን እያበራታታ ይህን ተፈላጊ ስብእና በመገንባቱ ረገድ ከፍተኛ ኣስተዋጾ ያደርጋል። ፓርቲዎችን በማቀራረብ ረገድ፣ የመፍትሄ ኣሳቦችን በማጠናቀር ረገድ፣ ለኣዲሲቱዋ ኢትዮጵያ የሚሆነውን ኣዲስ ሰውነት በመጠቆሙ ረገድ ከባድ ሚና ሊጫወት ይችላል። ከዚያ በተረፈ ደግሞ እኛ ተራ ዜጎች መሪዎቻችንን የማጎልበትና ወደ ህብረት የመግፋት እንዲሁም ስብእናቸውን የመገንባት ሃላፊነት ኣለብን።

የብዙ ኣፍሪካ ሃገሮች ችግር ይሄ ይመስለኛል። ታግለን በብዙ መስዋእትነት ኣንድ ኣምባገነን ከጣልን በኋላ መልሰን በሌላ ኣምባ ገነን እንተካለን። ሌላው ኣለም እየተሻሻለ ሲሄድ ይሄኛው ክፍለ ኣለም ወደ ኋላ የቀረበት ትልቁ ምክንያት የነጻነት ታጋዮች ራሳቸው በሚገባ ለኣመራር የሚበቃ ስብእና ሳያዳብሩ ወደ ስልጣን ስለሚመጡ ነው።ደቡብ ሱዳን ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ናት። ለብዙ ኣመታት የነጻነት ትግል ታግለው፣ ብዙ ደም በመፍሰሱ ዓለም ሁሉ እነዚህ ሰዎች ቢገነጠሉ ይሻላል ብሎ ፈርዶላቸው ተገነጠሉ። የዳርፉሩን እልቂት የማያውቅ፣ ያልሰማ ያለም ክፍል የለም። ያ ሁሉ ሆኖ ኣዲስ ኣገር ከመሰረቱ በኋላ ገና ኣንድ ጊዜ እንኳን ምርጫ ሳያካሂዱ፣ በህዝብ የተመረጠ መንግስት ሳይመሰርቱ፣ ከሁለት ዓመት ያልዘለለ እድሜ ያላትን ኣገር በጎሳ ከፋፍለው ማመስ ጀመሩ።

ያለ መታደል ሆኖብን በኣንዳንድ ኣፍሪካ ሃገራት የሚነሱ መሪዎች ስልጣን ላይ ከመጡ በሁዋላ ሁለት ነገር በጣም ይወዳሉ። ኣንደኛው ዝና ሲሆን ሁለተኛው ገንዘብ ነው። ሁለቱም እጆቻቸው ይዘዋል። ባንዱ ስልጣን በሌላው ገንዘብ። ዝናውን ወደው ገንዘቡን ችላ የሚሉ ቢሆኑ ትንሽ ይሻል ነበር። ነገር ግን ሁለቱንም በሃይል ስለሚወዱና ለዚህ የተሰጠ ስብእናቸው በውስጣቸው ስላልሞተ ክብ በሆነ ችግር ውስጥ እንድንወድቅ ኣድርጎናል።ኢትዮጵያዊያን በዚህ ላይ ልንነቃ ይገባናል። በተለይ የፖለቲካ ሰው መሆን የፈለጉ ወገኖቻችን፣ መሪ መሆን የሚሹ ወገኖቻችን በየጊዜው የባህርይ ለውጥ እያሳዩ በኣመለካከትና በሃላፊነት ስሜት እያደጉልን እንዲሄዱ እንሻለን። ከፍ ሲል እንዳልኩት እኛ ተራ ዜጎች ከውጭ ሆነን መፍረድ ብቻ ሳይሆን መሪዎቻችንን መንከባከብና ፍቅርን ክብርን ማሳየት ለፖለቲካ ቁርጠኝነታቸው ሃይል ይሰጣል።
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ!

[email protected]
ገለታው ዘለቀ

Image

መጀመርያ በዚህ የዓመቱ ምርጥ ብየ በምጠቅሰው ጥቅስ ልጀምር፦”የመሬት ላራሹ” ጩኸት ውጤቱ “መሬት ለነጋሹ” ሆኗል፤ ለገበሬው የታሰበውን መሬት ወያኔ ወሰደው። የዱሮ ንጉሣዊ ገዢዎቿ ቤተ ሰቦች ስለነበሩ በቊጥራቸው ማነስ ምክንያት እነሱን በማር ግብር ለማጥገብና በሰላም ለመኖር ቀላል ነበረ። የዛሬዎቹ ገዢዎች ብሔረ ሰቦች ስለሆኑ እነሱን ሁሉ በሚሊዮን ዶላር ማጥገብ መራቆትን አስከትሏል።” ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ (‘ዕርቅና ሰላም፤ የሕይወት ቅመም’ የካቲት 2006 ዓ.ም)
ወየኔዎች ወደ ሥልጣን ከመጡ በሗላ የአገሪቱን ሃብት ባገኙት አቅም እና ዘዴ ሁሉ በማራቆት ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ የትግራይ ሕብረተሰብ በታሪክ ላይ የሚኖሮው ግንዛቤ የተጣመመ እንዲሆን አድረገውታል። በርከት ያሉ እንሰሳዎች በተለያዩ ምክንያቶች ሆን መጀመርያ በዚህ የአመቱ ምርጥ ብየ በምጠቅሰው ጥቅስ ልጀምር፦”የመሬት ላራሹ” ጩኸት ውጤቱ “መሬት ለነጋሹ” ሆኗል፤ ለገበሬውየታሰበውን መሬት ወያኔ ወሰደው። የዱሮ ንጉሣዊ ገዢዎቿ ቤተ ሰቦች ስለነበሩ በቊጥራቸው ማነስ ምክንያት እነሱን በማር ግብር ለማጥገብና በሰላም ለመኖር ቀላል ነበረ። የዛሬዎቹ ገዢዎች ብሔረ ሰቦች ስለሆኑ እነሱን ሁሉ በሚሊዮን ዶላር ማጥገብ መራቆትን አስከትሏል።” ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ (‘ዕርቅና ሰላም፤ የሕይወት ቅመም’ የካቲት 2006 ዓ.ም)

ወየኔዎች ወደ ሥልጣን ከመጡ በሗላ የአገሪቱን ሃብት ባገኙት አቅም እና ዘዴ ሁሉ በማራቆት ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ የትግራይ ሕብረተሰብ በታሪክ ላይ የሚኖሮው ግንዛቤ የተጣመመ እንዲሆን አድረገውታል። በርከት ያሉ እንሰሳዎች በተለያዩ ምክንያቶች ሆን ብለው አጥቂዎቻቸውን ወይንም መሰሎቻቸውን ያታልላሉ። እንሰሳዎቹ በማታለል ዘዴ የሚኖሩበት ምክንያት የተለያዩ ምክንያቶች አሉዋቸው። ለምግብ፤ ወይንም እራሳቸው ከጥቃት ለመከላከል ሊሆን ይችላል።ይሁን እንጂ በተፈጥሮ እራሳቸውን እና ሌሎችን ሆን ብለው ለማታተለል/ለመዋሸት “የተሰሩ ፍጡሮች” ሰዎች ብቻ እንደሆኑ ያነበብኳቸው አንዳንድ የስነ ልቦና መጻሕፍቶች ይገልጻሉ።

የተለያየ ውሸት የተለያ ምክንያት ቢኖሮውም፡ ዋሾች አድማጭ ፈላጊዎች ናቸው። አታላዮች/ዋሾዎች እንደ እንደተሰጥዎአቸው የማጭበርበር፤ የመዋሸት ወይንም ማራኪ የንግግር ችሎታቸው ይለያያሉ። የተከታዮቻቸው ብዛትም አንደሚጠቀሙበት የማጭበርበር ስልት ይለያያል። ተራ ዋሾዎች ካደጉበት የውሸት ባሕሪ በመነሳት ሕዝብን የመምራት ፍላጎት እያዳበሩ በሄዱ ቁጥር፤ በመንግሥት፤ በፖለቲካ፤ በሃይማኖት ግብተው መሪነቱን ከያዙ፤ አደገኛ የውሸት ባሕሪያቸው በመጠቀም ሕዝቡን በውሸት ጐዳና በመምራት፤ “ዋሾ ማሕበረሰብን” ይገነባሉ።

እራሱን ያታለለ ማሕበረሰብ “የሕሊና ጎዶሎ/ሃንዲካፕ” ነው። ሌላ ቀርቶ በየጽሑፎቻችን ላይ የሚታዩ ግድፈቶች/ የቃላት ስህተቶች ልብ ሳንላቸው አልፈን ከታተሙ በሗላ ነው ስህተቶቹ ግልጽ ሆነው የሚታዩን። የዋህ ሕሊናም በአታላዮች አስተሳሰብ ሲጠለፍ እራሱን መፈተሽ ስለሚያቅተው፤ ከመሪዎቹ የሚነገሩት ሁሉ እውነት ስለሚመስለው፤ እሱም በውሸቱ ዘመቻ እየተካፈለ በሄደ ቁጥር እየዋሸ እንደሆነ አይታወቀውም። በመጠጥ ከሰከረ ይልቅ፤በውሸት የሰከረ ማህበረሰብ አስቸጋሪ ስለሚሆን (ዲናያል/ክሕደት) እውነታውን ለማስጨበጥ ጊዜ ስለሚፈጅ፤ የእውነት አስተማሪዎች ከዚህ ማሕበረሰብ ጋር ከፍተኛ ግብግብ ይገጥማቸዋል።

ይህ አሳዛኝ ባሕሪ ኢትዮጵያ ውስጥ በባሰ ደረጃ በወያኔዎች ዘመን ተከስቷል። የ ‘ወያኔ ትግሬ’ የውሸት ባሕሪ በታሪካችን፤በባሕላችን፤ በአርበኞቻችን እና በሉዓላዊነታችን ክብር ላይ ጥቃት አድርሷል። ጉዳቱ በጣም ከፍተኛ ነው።

ለዚህ ጹሑፍ መነሻ የሆነኝ፤ ሶሞኑን ‘ትግራይ ኦን ላይን’ በተባለው “ፍሎሪዳ” መሰረቱ ያደረገ የወያኔዎች ድረገጽ “Woyane Tigray: 39 Years and Still Standing” በሚል ያስነበበውን መነሻ በማድረግ ነው። (ጸሐፊው ሞቡቱ ሴሰ ሴኰም ሆነ ጋዳፊ ከወያኔ ዕድሜ በላይ እንደገዙ አላወቀም።

“እንደ ጋዳፊ
መለስን በጥፊ ፤
ሳንፈልጋቸው
ሃያ አመታቸው!”

ተብሎ የተጨፈረለትን የወያኔ ስርዓት አልሰማም መሰለኝ።) ርዕሱን በዚሁ ልምልስ እና ጸሓፊው በበላይ ዘለቀ እና በአሉላ መካካል ያለው ልዩነት ያነጻጸረበትን የውሸት ክስ እንመለከት።ከብርሃነ ካሕሳይ በሚል የተጠቀሰው ርዕሰ የጻፈው ጸሐፊ የዓይጋ ድረገጽ አዘጋጅ ወይንም የትግራይ ኦንላይን አባል አዘጋጅ እንደሆነ ይገመታል።ቢሆንም ባይሆንም ቁም ነገሩን ብቻ እንመልከት።

“…The warrior of Dogali, Gundet and Gura, is not receiving the accolade he rightly deserves simply because he happens to be a Tigrayan. Reverence for Belay Zeleke, who fought the Italians in Gojjam for a brief period, appears to be far greater than the hero of Africa. Unfortunately, the courageous Belay Zeleke was subsequently hanged by Emperor Hailesellaise upon his return from Bath, England, where he had resided after fleeing the country, leaving the people at the mercy of the Italian occupiers.” http://www.tigraionline.com/articles/wo … years.html (By Berhane Kahsay
Tigrai Onlne – February 09, 2014)

ይህ ውሸት ተደጋግሞ በወያኔ ትግሬ መሪዎች እና ተኮልኳሊዎቻቸው ተነግሯል። ባለፈው ወር የዶጋሊ በዓል ማክበር ሲገባ፤ ወያኔዎች ሳያከብሩት በዝምታ አልፈውታል። በዚህ የተነሳ ወዳጄ አቶ ብርሃኑ ሰፋ ያለ ቅሬታው ኢ ኢ ዲ ኤን በተባለ ማሕበራዊ መድረክ ለተቃዋሚውም ሆነ ለወያኔዎች ለምን አንዳልተከበረ ቅሬታው ገልጿል። ቅጁም ለእኔ አስተላልፎልኛል። ድሮ ደርግ ምፅዋ ላይ /ዶጋሊ ላይ ስለ አሉላ ያዘጋጀው የሲምፖዚየም ንግግር በመጽሐፍ ተጠርዞ አንዳነብበው ልኮልኝ አንብቤ አንድ ነገር አንዳዘጋጅ ተማጽኖኝ ነበር። ንባቡ ገና ሳልጀምር ወያኔዎች ከላይ የተመለከተው ሚዛን ያልጠበቀ የክስ እሮሮ በራሳቸው ከማድረግ ይልቅ በሌለው ላይ ክስ ሲያወርዱ አንብቤ ነው ይህ ድንገተኛ መልስ ለመጻፍ የተነሳሳሁ።

ወየኔዎች የውሸት ክስ፤ስም ማጥፋት፤ ክሕደት የድርጅታቸው ባሕርያዊ ቋሚ መለያቸው ነው። በጣም በርከት ያሉ መጽሐፍቶች የአጼ ዮሐንስም ሆነ የራስ አሉላ ታርክ እና ሞገስ ‘አማራ ታሪክ ጸሐፊዎች”’ ብለው ወያኔዎች በሚጠሯቸው የኢትዮጵያ ታሪክ ጻሀፊዎች የጻፏቸው እያንኳሰሱ፤ ዛሬ ወያኔዎች ከ22 አመት ንግሥና በሗላ ገንዘቡ፤ሕትመቱ፤ሳነሱሩ፤ውሸቱ ፤ብዕሩ፤መዛግብቱ፤ዩኒቨርሲቲው እና ምርምር ተቋማቱ በእጃቸው ቁጥጥ ባለበት ዘመን ምንም ሳይጽፉ በሃያ ሁለት አመት ውስጥ ስለ ዮሐንስ አንድ መጽሐፍ (በትዕቢት የተቆለለ ፤በውሸት የተበረዘ) የገብረኪዳን መጽሐፍ ብቻ ነው። ወደ ሃውልት ስንገባም፤ ወየኔዎች በአገሪቱ ስም ከውጭ አገር ዕዳ እየተበደሩ ወደ ኪሳቸው ከማግበስበስ እና ልጆቻቸው ወደ ውጭ አገር እየላኩ ከማስተማር እና እራሳቸውም በውድ ገንዘብ እየገዙ ዲግሪ ከማግኘት በስተቀር ለንጉሡም ሆነ ለራስ አሉላ ሃውልት ማሰራት ሲችሉ ወይንም ሕዝቡን አሰባስበው (እርዳታ እንኳ ካስፈለገ) ከማስሰራት ይልቅ እስካሁን ደቂቃ ድረስ ምንም የሰሩላቸው ሃውልት ወይንም መታሰቢያ የለም።

ስለ አሉላ ተሰራ የተባለው ሃውልት “የተቀመጡበት ፈረስ የአህያ ምስል በመያዙ፤ሕዝቡ ተቃውሞውን በማሰማት ሌላ የፈረስ ምስል የያዘ ሃውልት እስኪሰራ ድረስ በአቡጀዲ ሸፍነውት አንደነበረ ይታወቃል።

አንዳንዶቹ የሚሉት ያህያ ምስል አንዲቀመጡ የተደረገው ሆን ተብሎ በሻዕብያ አፍቃሬ ኤርትራዊያን ወያኔዎች ሴራ ምክክር እንዲቀረጽ አንደተደረገ በሃሜታ መልክ ይሰማል።

በሃያ ሁለት አመት ለአጼ ዮሐንሰም ሆነ ለአሉላ ይህ ነው የሚባል አጥጋቢ መታሰቢያ አንዳልሰሩላቸው የምከራከረው በመረጃ ነው። አማራ አንዲህ አደረገ ፤ያለፉት ጸሐፊዎች የንጉሳችን ታሪክ አልጻፉም፤ ሃውልት አልተሰራላቸውም… እያሉ በውሸት እስካሁን ድረስ የወያኔ ትግሬዎች የትግራይን ሕዝብ ሲያታልሉ 22 አመት አልፏቸው ስለ አሉላም ሆነ ስለ ዮሐንስ የሰሩት አንደም መታሰቢያ አይገኝም። ይልቁንስ ወያኔዎች “ለአሉላ ወይንም ለዮሐንስ” ሃውልት ነፍገው ኤርትራ ምድር ድረስ ሄዶ፤ ምፅዋ እና ሳሕል የኢትዮጵያን ሰራዊት የወጋ በክሕደቱ ዘመን ከጠላት (ሻዕቢያ) ጋር ተሰልፎ የወጋን የራሳቸው ታጋይ ለሆነው “ሓየሎም አርአያ “ (ሐዱሽ አርአያ) ሽሬ አውራጃ ውስጥ ሃውልት አቁመውለታል። ታዲያ

“…The warrior of Dogali, Gundet and Gura, is not receiving the accolade he rightly deserves simply because he happens to be a Tigrayan. Reverence for Belay Zeleke, who fought the Italians in Gojjam for a brief period, appears to be far greater than the hero of Africa.”

በማለት የወያኔ ቱልቱላዎች በታሪክ ጻሀፊዎች እና ባለፉት ገዢዎች ላይ የትግሬ እና የአማራ አርበኞችን እያነጻጸሩ የሚከስሱት ዘረኛ ክስ ከመክሰስ በፊት ሁሉም ነገር በእጃቸው ባለበት ሃያ ሁለት አመት እራሳቸው ያልሰሩትን ሌሎች አንዲሰሩላቸው መጠበቅ እና መክስስ አስገራሚ ክሰ ነው?

ለመታሰቢያ የቆሙ ከጣሊያን ወራሪዎች ጋር ተዋግተው በክብር የተሰውት የነ ደጃዝማች አፈወርቅ ፤የነ አቡነ ጴጥሮስ ፤የነ አሉላ፤ የእነ ምኒሊክ ወዘተ መታሰቢያ ሃውልቶች እያፈራረሰ እና እንዲፈርስ ዘመቻ እያካሄደ ያለው የሃያ ሁለት አመት አሳፋሪ ታሪክ የታቀፈው ማን ሆኖ እና ነው ማቆሚያ የሌለው ሃያ ሁለት አመት “የሕፃናት ልቅሶ እና ክስ” እየተለቀሰ ሌላውን ወገን ተወቃሽ የሚሆነው? ወያኔዎች ትንሽ የአደብ ሓፈረት የሚባል የሕሊና ገዢ እንዴት አንደተለያቸው ይገርመኛል? በሃይለስላሴም ሆነ በደርግ ዘመን ስለ አሉላም ሆነ ስለ ዮሐንሰ ጀብዱ አንዳንጽፍ ተከለከልን ካላችሁ፤ ውጭ አገር ሲኖሩ የነበሩ በርካታ የትግሬ ምሁራን የማን ጎፈሬ ሲያበጥሩ ኖሮው ነው (ከዘውዴ ገ/ስላሴ በቀር) አማራው እንዲጽፍላቸው የጠበቁት እና ተከሳሽ የሚያደርጉት? ያስ ተከድኖ ይብሰል፡ – ሃውልት አልቆመላቸውም፤ ታሪካቸው አልተጻፈም .. ወዘተ… የምትሉት አሰልቺ ልቅሶ ‘ሃያ ሁለት አመት’ ሙሉ ከማልቀስ እና ከመክሰስ ያለፈ ስራ ምን ሰራችሁ? እስኪ ንገሩን? ምን ሃውልት ሰራችሁ? የሐለፎም ሓውልት? የወያኔ ተጋዮች ሃውልት? ለነሱ ከማቆም ይልቅ ለክሳችሁ መነሻ የሆነው የወላጆቻችን ጀግንነት እና ንግሥና አማራዎች ነጠቁን ብላችሁ በረሃ ለመሄድ ከገፋፋችሁ ምክንያት አንዱ ከሆነ የአሉላም ሆነ የዮሃንስ ሃውልት ቅድሚያ ለምን አልሰጣችሁትም? የአሉላ እና የዮሐንስ ገድል ይበልጣል ወይስ አሉላ እና ዮሐንስ ያስከበሩትን ድምበር እና ባሕር ያስደፈሩ እና የዘጉ የወያኔ ታጋዮች ገድል? የአሉላም ሆነ የዮሐንስ ገድል የቀበረ እና በባንዳ ተልዕኮ የተሳተፉትን የጎሳ ታጋዮች ገድል ጎልቶ በበላይነት አንዲታይ እያደረገ ያለው ማን ነው? ኢትዮጵያዊያኖቹ ዮሐንስ እና አሉላ መታሰቢያ ሳይቆምላቸው፤ ለጎሳ ታጋዮች ለምን ቅድሚያ ተሰጣቸው?
የወያኔ ውሸት ታሪክን የመበረዝ እና የማጣመም ባሕሪ በምን ዓይነት የአጻጻፍ ዘዴ ቢጻፍ የውሸታቸው ክምር አንዴት መግለጥ እንደሚቻል ሳስበው ይጨንቀኛል። በዶጋሊ፤ጉንደት፤ጉራዕ፤ዓድዋ፤ባድመ፤ዓድዋ… የተደረጉ ጦርነቶች የትግሬዎች የመከላከል ታሪክ እና ጀግንነት ብቻ ነው እያሉ ያለ ምንም ሐፍረት ወይንም ዩልኝታ የሚገልጹት ባሕሪያቸው ሳስበው ለሕሊና ይከብዳል። የዚህ ውሸት ማቆሚያው መቸ እና የት ይሆን?

የዶጋሊ፤የሳሐቲ፤ወዘተ …. ወዘተ… ብዙ ኢትዮጵያዊያን የተቀላቀሉበት አንዳንዱም በመሪነት የመሩዋቸው ታላላቅ ውግያዎች ውጤት እንጂ የትግሬዎች ብቻ አይደለም። ድሉ እና ሱታፌው የትግሬዎች አንጂ የተቀሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሱታፉ አልነበረም፡ የሚሉት ተዳጋገሚ ውሸታቸው በመጽሐፍም በንግግራቸውም በየስብሰባውም እስኪሰለቸን ድረስ ደጋግመውታል። ሃቁ ግን እነሱ እንደሚሉት ሳይሆን በተጠቀሱት ጦርነቶች የተሳተፉት ትግሬዎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም የተሳተፉበት ውጊያ እና ድል ነበር። መረጃውም ቆየት ብየ አቀርባለሁ። ይህ መረጃ ላንዴ እና ለመጨረሻ ውሸታቸውን የሚያቆም በመሆኑ መረጃውን እንድትጠቀሙበት በጥንቃቄ አስቀምጡት።

መረጃውን ከመጥቀሴ በፊት ማለት የምፈልገው ነገር፤ መረጃው ካነበቡት በሗላ አንዳንድ ወያኔዎች፤ “ምንም እንኳ ከሌሎች አካባቢዎች የመጡ ሰራዊቶች በዶጋሊ፤ በጉራዕ…ወዘተ ይኑሩ እንጂ አብዛኛው ተዋጊ የትግሬ ሰራዊት ስለነበር፤ ድሉ የትግሬ ሰራዊት ነው፡ የሚሉ የወያኔ ጐሰኞች ሊኖሩ ይችላሉ።ለነዚህ የምሰጠው መልስ “ዓድዋ ላይ የተሳተፈው ተዋጊ ሠራዊት፤ አብዛኛው ትግሬዎች ሳይሆኑ የሸዋ የንጉሥ ምኒሊክ ሠራዊቶች ናቸው። ሌላ ቀርቶ የወያኔ ወዳጅ የሆነው አይሁዳዊው ‘ኤሪክ ሓጋይ’ “አሉላ” በተባለው መጽሐፉም የትግሬ ሰራዊት እጅግ ጥቂት ስለነበረ አሉላ የሰራው የውግያ አስተዋጽኦ ጎልቶ የሚታይ አልነበረም። ኢሚንት ነው። በማለት መስክሯል። በዚህ ክርክር ከገባን “ከራስ መንገሻ (አሉላ) ሸራዊቶች” ይልቅ ከሌሎች ኢትዮጵያ መንደሮች የመጣ በተለይም ከሸዋ በብዛት የተሳተፈ ሠራዊት ስለነበር፤ የዓድዋ ድል ‘የሸዋ ሠራት ድል’ መሆን አለበት ሊባል ነው ማለት ነው?” ዋናው የውሸት ቀፎ የሆነው የ ‘ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ’ ድርጅት፤ በድርጅቱ ሁለተኛ ጉባኤ (1975) ያጸደቀው ውሳኔ አንዲህ ይላል “በአገራችን የሰሜን ጦርነቶች በዶጋሊ፤ጉንደት፤ጉራዕ… የተካሄዱ ጦረነቶችና ድሎች የኤርትራ ሕዝቦች እና የትግራይ ሕዝቦች ድል ነው”። ሲል በ13ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በእነ አምደጽዮን (ከሸዋ እየገሰገሱ) እና በመሳሰሉት የድሮ ነገሥታት ከሩቅ ያገሪቱ ግዛቶች እየተወረወሩ ወደ “ሓማሴን ምድር ወይንም ወደ ባሕረ ምድር” (ኤርትራ) በመሄድ ከቱርኮች እና ከመሳሰሉ ወራሪዎች ተዋግተው ጠላት ድል የመቱትን ሁሉ በመደበቅ፤በአካባቢው የተደረጉ ጦርነቶች የትግሬ ጀግኖች ውጤት እያሉ ሚዛን ያጣ ትምክሕት በማሰራጨት አዲሱን የትግራይ ትውልድም ያንን ውሸት እየተቀበለ በዛው ትምክሕት እየተወጠረ መራመድ ጀምሯል።
አሁን ወደ መረጃዬ ልሂድ።

«—-ዘመናዊ የካራቢነር ጠመንጃና መድፍ የጨበጠው የግብፅ ጦር ወደትግራይ አምርቶ የመረብን ወንዝ ተሻገረ።በኅዳር 7 ቀን 1875 ከዚህ ወንዝ አጠገብ ጉንደት ከተባለች ሥፍራ ላይ በንጉሠነገሥት ዮሐንስ 4ኛ የተመራ የኢትዮጵያ ሠራዊት መንገድ ዘጋበት።ንጉሡ ሠራዊቱን በሁለት ከፍሎ ፤ አንዱን ክፍል ራሱ፤ ሁለተኛውን ክፍል በዚያን ጊዜ የተመሰከረለት ጀግና የነበረው ራስ አሉላ እንዲመራው አደረገ። ሁለቱም የኢትዮጵያ ክፍለ ጦር ከተለያየ አቅጣጫ ደወ ግብፁ ምሽግ ተንቀሳቀሱ። የጉንደት ጦርነት ሙሉ ቀን ፈጀ። ከምሽቱ ላይ ድሉ ለኢትዮጵያውያን ማድላቱ እየለየ መጣ። አብዛኛቹ በጀግንነት የተዋጉ ግብፃውያን ከትግሉ አውድማ ላይ የወደቁ ሲሆን፣ ከነዚህም ውስጥ አራኪል ቤይ እና ሻምበል አረንድሩፕ ያገኛሉ። ከፊሉ ተማረከ፣ አምልጦ ምፅዋ ሊገባ የቻለው በጣም ጥቂት ነው።

« ከዚህ ውድቀትም በኋላ ከዲቭ እስማኤል በኢትዮጵያ ላይ ቀጣዩን ዘመቻ ለመክፈት ዝግጅት ማድረግ ጀመረ። ለቀጣዩ ጦርነት ካሁኑ የበለጠና የተሻለ ትጥቅ ያለው ሠራዊት ለማዝመት ወሰነ። ላሁኑ ዘመቻ 20,000 ወታደር አዘጋጅቶ በእጁ የሚገኘውን የተሻለ መሣሪያ ሁሉ አስታጠቀው። እስማኤል ለአዲሱ ዘመቻ በጀርመን አገር በወታደራዊ ሥልጠና የተመረቀውን መኮንን ሙላይ ሐሰን ፓሻን አዛዥ አድርጎ ሾመው። ከሱም ጋር ሌሎች የግብፅ የጦር መሪዎች አብረውት የዘመቱ ሲሆን፣ ከነዚህም አንዱ ዝነኛው ራቲብ ፓሻ ነበር።

በታኅሣሥ ወር 1875 የከዲቩ ጦር ምፅዋ ላይ አርፎ በዝግታ ወደ ማህል ኢትዮጵያ መንቀሳቀስ ጀመረ። በየካቲት 1876 ከመረብ ወንዝ ተጠጋ።
« ለዚህ የግብፅ ወረራ ምላሽ ዮሐንስ 4ኛ በሞሐመዳውያን ላይ “የመስቀል ዘመቻ“ አዋጅ አስነገረ። ንጉሡ ከጎጃምና ከሸዋ የማጠናከሪያ ኃይል እንዲመጣ አድርጎ ፣ጠቅላላው የሠራዊቱ ቁጥር 60,000 ደርሶ ነበር። ሁለቱ ሠራዊቶች በመጋቢት ወር 1876 ጉራዕ ላይ ተጋጠሙ። ግብፆች ምሽጋቸውን ዙሪያውን በጉድብ ሰንሰለት ስላጠሩት የኢትዮጵያውያኑን ጥቃት ለመከላከል አመችቷቸው ነበር። ከግጥሚያው መጀመሪያ ላይ ስለቀናው ተደፋፍሮ ሙላይ ሐሰን በልምድ የበሰለውና ሽማግሌው ወታደር ራቲቭ ፓሻ ተው እያለው ጠላቱን በግላጭ ገጥሞ እደመስሳለሁ ብሎ ከምሽጉ ወጣ። ይህ ውሳኔ ለግብፆች መጥፊያቸው ሆነ። የኢትዮጵያ ወታደር በቁጥሩ ከወራሪው ጦር እጅግ ከፍ ያለ ነበርና የውጊያውን ሰልፍ ጥሶ እየተወረወረ ከጠላቱ ምሽግ ውስጥ ገባ። በአጭር ጊዜ ውስጥ ውጊያው ወደ መተላለቅ ተለውጦ የግብፅ ጦር በድንጋጤ ተውጦ ፈረጠጠ። ሙላይ ሐሰን ፓሻ ሩጦ ለማምለጥ ሲሞክር ተይዞ ከንጉሡ ፊት ቀረበ። ንጉሡም ድል የሆነበትን ቀን እንዳይረሳው ሲል ከክንዱ ላይ ሁለት መስቀል እንዲተኮስበት አደረገ። በግብፅና በኢትዮጵያ መካከል የሰላም ውል ከተደረገ በኋላ ከዲቭ እስማኤል ፣ ሙላይ ሐሰን ፓሻና ሌሎችም በጉራይ ጦርነት ላይ ከሱ ጋር የተማረኩትን ከፍተኛ መኮንኖች ማስለቀቂያ ከፍሎ አስፈታቸው።»(ገጽ 289 እስከ 299፣“የኢትዮጵያ ታሪክ ከመጀመሪያው እስካሁኑ ዘመን፣ጸሐፊዎች፦ አንድርዜይ ባርትኒስኪ እና ዮዓና ምንቴል-ኒየችኮ” ተርጓሚ፦ ዓለማየሁ አበበ 2003)

ስለሆነም በጉራዕ፤በጉንደት፤በስዋኪን፤በዶጋሊ፤በዓድዋ፤በማይጨው፤መመሳሰሉት ጦርነቶች እና በቅርቡም የትግሬው ወያኔ እና የኤርትራው ሻዕቢያ በጫሩት 70,000 የሚገመት ተጠያቂ የሌለው ሕይወት የበላ የጥላቻ ጦርነት ከሁሉም ወይንም ከከፊል የኢትዮጵያ ግዛቶች የሚኖር ሕዝብ የተካፈለበት ጦርነት ነበር። ወያኔዎች በሁለተኛ ጉባኤያቸው የኛ የትግሬዎች ገድል ብቻ ነው ብለው ያሉት በውሸት የተመሰረተ “የትግራይ ጦር ብቻ” የተሳተፈበት ጀግንነት ያሉትን ውሸትም ሆነ፤ የወያኔ ታሪክ ጸሐፊዎች ነን የሚሉን ትምክሕተኞቹ የትግሬ ብሔረተኞች በመጽሐፍቶቻቸው የሚዋሹት እና የሚመኩባቸው የተጠቀሱት የትግሬ ጦር ውሎ ጀብዱ ሁሉ የትግሬ ብቻ ሳይሆን ጦሩ በዚያን ዘመን ኢትዮጵያ ተብላ በምትታወቀው አገር ይኖሩ የነበሩ ዜጎች በጦርነቱ ተካፋይ እንደነበሩ ከላይ ለመከራከሪያ ያቀረብኩት የመረጃ ሰነድ ማለትም “የኢትዮጵያ ታሪክ ከመጀመሪያው እስካሁኑ ዘመን፣ጸሐፊዎች፦ አንድርዜይ ባርትኒስኪ እና ዮዓና ምንቴል-ኒየችኮ” ተርጓሚ፦ ዓለማየሁ አበበ 2003 ያስረዳል።

የትግሬዎች እና የተጠቀሱት የአካባቢ ተሳታፊዎች የቁጥር ልዩነት ይችላል ወይ? አዎ ምናልባት ሊኖረው ይችላል። ያም በእርግጠኝነት ይህ ነው ማለት ባይቻልም ካራት ወይንም ከሦሰት ክ/ሃገራት የተውጣጡ ተዋጊዎች በቁጥር አነስተኛ ማሕበረሰብ ከነበረው ከትግራይ ጦር ሲነጻጻር ሊበዛ ወይንም እኩል ሊሆንም ይችልም ይሆናል። የጉራዕ/ጉንደት ጦርነት ግን ከጎጃምና ከሸዋ በብዛት የዘመተ መኖሩን በግልጽ ያሳያል። ጎንደርና ወሎ ያልተጠቀሱበት ምክንያት ሁለቱም በንጉሡ ቀጥተኛ ቁጥጥር ሥር የነበሩ በመሆኑ ተሳትፎአቸው ግልጽ ስለሆነ ነው።

አሁን መረጃው ሰጥቻለሁ። የወያኔ ትግሬ ጸሐፍት ጉረኞች በየመጽሕፍቶቻችሁ እና በየቃለ መጠይቃችሁ የምትነዙት አጉል ጉራ እና ታሪክ አደፍራሽነታችሁ ረገብ አንድትሉ በግራ ቀኝ የተጻፉ የታሪክ ሰነዶች አንብቡ። ለዚህም ነበር አፄ ዮሐንስ ‘የትግሬ ልጅ ሆይ” ሳይሆን ሲሉ የነበሩት ለጦርነት ሲዘጋጁ “የኢትዮጵያ ልጅ ሆይ” ነበር እያሉ መላውን ግዛታቸው ያለው ሕዝብ ለጦርነት ጥሪ ሲያደርጉ የነበሩት። ለዚህም ነበር “የኢትዮጵያ ልጅ ሆይ ልብ አድርገህ ተመልከት። ኢትዮጵያ የተባለች አንደኛ እናትህ ናት፣ ሁለተኛ ዘውድህ ናት፣ ሦስተኛ ሚስትህ ናት፣ አራተኛ ልጅህ ናት፣ አምስተኛ መቃብርህ ናት። እንግዲህ የእናት ፍቅር፣ የዘውድ ክብር፣ የሚስት ደግነት፣ የልጅ ደስታ፣ የመቃብር ከባቲነት እንደዚህ መሆኑን አውቀህ ተነሣ።“(አፄ ዮሐንስ ፬ኛ) ሲሉ የነበሩት።

ወያኔዎች የትግራይ ወያኔ ብሄረተኞች ከንጉሥ ዮሐንስ “የኢትዮጵያዊነት” ትርጉም ምን ማለት አንደሆነ ሊማሩት አልፈቀዱም። አለማፈራቸው ዛሬ ደግሞ ይባስ ብለው “ማንነት” ትግራዋይነት አንጂ “ኢትዮጵያ” የሚባል ማንነት የለንም መላት ጀምረዋል። ንጉሥ ዮሐንስ እያሉን ያሉት ግን “ኢትዮጵያ ማንነትህ ናት” -ኢትዮጵያ የተባለች አንደኛ እናትህ ናት፣ ሁለተኛ ዘውድህ ናት፣ ሦስተኛ ሚስትህ ናት፣ አራተኛ ልጅህ ናት፣ አምስተኛ መቃብርህ ናት። እንግዲህ የእናት ፍቅር፣ የዘውድ ክብር፣ የሚስት ደግነት፣ የልጅ ደስታ፣ የመቃብር ከባቲነት እንደዚህ መሆኑን አውቀህ ተነሣ።” ሲሉ በወርቃማው ‘ኢትጵያዊ ማነንት’ ትርጉማቸው ተርጉመውልን ቢሄዱም “የወያኔ ባንዳዎች” ወደ ቁልቁል ወደ መንደራቸው በመሸማቀቅ “ትግራዋይነት” አንጂ ኢትዮጵያዊ የሚባል ማንንት የለም፤ በማለት ወደ “ትግሬነት” ወደ “ኤርትራዊነት” ማንነት ወደ እሚሉት ደደቢታዊ እና ናቕፋዊ የግንጠላ አዝማሚያ እና መንደርተኛነትን አጥብቀው ማማንዠክ ይዘዋል።

የትግራይ ኦን ላይን ውሸታሞች በአማራ ሕብረተሰብ እና አርበኞች ላይ ያላቸው የጥላቻ መንፈስ ከኤርትራዊያኖቹ የባሰ ጥልቅ እንደሆነ ልብ ያለው በበሰለ ሕሊና የተከታተላቸው ታዛቢ የሚመሰክረው ቢሆንም ዛሬም ከሃያ ሁለት አመት በሓላም ጥላቸው እና ትንኰሳው ስላልበረደላቸው፤ በትግሬው አሉላ እና በአማራው በላይ ዘለቀ (አማራ እና ትግሬ የሚለው በሽታቸው ሲያወዳድሩ) መካከል ልዩነት ፈጥረው “አማራዎች” የአሉላን ክብር እንድያንስ አድርገዋል፡ እያሉ የአማራ ጸሐፊዎችን የሚከስሱት ውሸት እራሳቸው በራስ አሉላ ላይ እያደረጉት ያሉት ደባ እንዳይጋለጥ የሚያደርጉት ተንኰል ነው። የሚከተለውን ጉድ አንብቡ፤

“Tigrai Rep. officially disowns the indomitable lion of Dogali, Ras Alula” በሚል ርዕስ ወንድማችን ጌታሁን በቀለ የዘገበውን እንመልከት።

The Horn Times Newsletter, Dec 2, 2012
By Getahune Bekele

“ The great Abyssinian chief Ras Alula is at present a person of much interest to the Italians, and the Reforma is publishing a sketch of his life, in the course of which it is stated

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ በቅረቡ ወደ ሚዲያ የመጡት የኤርትራው ወዲ ኢሳያስ አፈወርቂ በሚዲያ ቀርበው አንድ አንድ ነገር በማለታቸው፤ ከማን እናንሳለን በሚል ነው የሚሉ ሰዎች ጋር መስማማት የለብንም፡፡ አጋጣሚ ነው ብለን ማለፍ ካልፈለግን አጋጣሚ ባይሆንም አጋጣሚውን ለእኛም እንድ አንድ “እውቀት” የሚጨምር ነገር ልናገኝበት የምንችል አጋጣሚ አድርጎ መውስድ ግድ ይለናል፡፡ እውቀት የሚለውን ነገር ግን ልብ ልንለው የሚገባ ነው፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ምላሽ ተከትሎ ብዙ አስተያየት የተሰጠ ቢሆንም፣ የግል ዕይታዬን ማካፈል የተደጋገመ ቢሆን ጥሩ ነው ብዬ አመንኩ፡፡ ምክንያቱም በመሬት ላይ ካለና ከምናየው እውነትና እውቀት ጋር የተጋጨ ስለመሰለኝ፡፡
የቡድን አመራርን በተመለከተ የቡድን አመራር ነው ለሃያ ዓመት በፓርቲያችን ያለው ማለት አቶ መለስ እያሉም አመራር ላይ ነበርን ሊሉን ከሆነ ተሳስተዋል፡፡ ከህወሃት ክፍፍል በፊት (እነ ሰዬ፣ ገብሩ፣ ተወልድ፣ ወዘተ) በሚመክሩበት አጀንዳ እኛም ነበርን ሊሉን አይችሉም፡፡ በዚያን ጊዜ የቡድን አመራር በህወሃት ውስጥ እንደ ነበር እናውቃለን፣ ይህ በኢህዴግ ውስጥም ዘልቆ ገብቶ ነበር ማለት አይቻልም፡፡ ይልቁንም አንድ አንድ የህወሃት ሰዎች በየክልሉ ተቀምጠው የህወሃት ውሳኔ ያስፈፅሙ ነበር፡፡ ከህወሃት ክፍፍል በኋላ ነገሮች እንደተቀየሩ እሙን ነው፡፡ ከህወሃት የቡድን አገዛዝነት ወደ አቶ መለስ ዜናው እጅ ስልጣን ተጠቃሎ ነው የገባው፡፡ ለዚህም ነው አቶ መለስ ዜናዊን “ጠቅላይ” የሚባሉት፡፡ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ቦታውን ከያዙት በኋላ በጠቅላይነት የሚያማቸው የለም፡፡ እንደ እኔ ዓይነቱ ወደ ቡድን አሰራር ገብተዋል የሚል ግምት የያዝን አለን፡፡ ሌሎች ደግሞ ወደቀድሞ ቦታ ተመልስው ህወሃት ነው ከጀርባ ሆኖ ማርሽ የሚቀይረው ብለው ይጠራጠራሉ፡፡ እንዲህ ያለህ የተምታታ ግምት ስለአለ ነው በዘዴ በእርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትር ነዎት?የሚል ሽንቋጭ ጥያቄ ያስነሳው፡፡
ኢህአዴግ በግልፅ እንደሚናገረው ተግባራዊ ነገር አድርጊያለሁ ብሎ የሚያምነው ከተሃድሶ በኋላ እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ከተሃድሶ በኋላ ደግሞ አቶ መለስ ጠቅላይ የነበሩበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት አቶ ኃይለማሪያምም ሆኑ ሌሎች ሰዎች ሹመት እንጂ ስልጣን አልነበራችሁም፡፡ ለምሳሌ አቶ ኃይለማሪያም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ነበሩ፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ጠቅላዩ የነበራቸው መረጃ በሙሉ ነበረኝ ምክንያቱም የቡድን አመራር ስለምንከትል ብለው አይዋሹኑም፡፡ ቢሉም በፍፁም አናምኖትም፡፡ በዚያ ደረጃ ተተኪ ልሆን እችላለሁ ብለው ዝግጅት እንዳልነበሮት የሚያሳብቀው እውነት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ድንገተኛ ሞት ቦታውን ሲይዙ ከሚሰጡት መግለጫ ለመረዳት የሚቻል ነበር፡፡ ለማነኛውም በቅጡ የኢህአዴግ የቡድን አመራር እንዲኖር ማድረግ ተገቢ ቢሆንም ወሳኝ ስብዕና ደግሞ ከጠቅላይ ሚኒስትር የሚጠበቅ መሆኑን ተረድተው የቡድንም የግለሰብም ወሳኝነት ተመጣጥነው የሚሄዱበት መስመር የግድ እንደሚል ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ በነገራችን ላይ የአሜሪካው ፕሬዝደንት በግላቸው እንደፈለጋቸው አይወስኑም፡፡ ይህን ለመረዳት ቢንላደንን ለመያዝ የተደረገውን ዘመቻ እንዴት በቡድን እና እንዴት በግል ኃላፊነት ወስደው እንደወሰኑ የሚያሳየውን ፊልም ይመልከቱት፡፡
ቴሌ እና የሚታለብ ላም
ይህን በተመለከት ዶክትር ካሱ ኢላላ ብለውት እስከ ዛሬ ድረስ ካደረጉት ስህተት እንደ አንዱ የሚቆጠር የነበረ ነው፡፡ ኢህአዴግ አፍ እንጂ ጆሮ የለውም የሚለውን በሚያጠናክር ሁኔታ ቃል በቃል ሲደግሙት በግሌ አዝኛለሁ፡፡ ምንም ጥርጥር የሌለው ነገር ቴሌ “በመንግሰት እጅም” ሆኖ አትራፊ ነው፡፡ ቴሌ አሁን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በነገሩን መረጃ መሰረት በመንግሰት እጅ ሆኖ 6 ቢሊዮን ብር ትርፍ ለልማት ያውላል ብለውናል፡፡ ያልገባቸው ነገር ግን ቴሌ በግል ይዞታ ቢሆንም ከዚህ ሶሰት እጥፍ የሚሆን ትርፍ ሊያተርፍ እንደሚችል ነው፡፡ ከዚህ ትርፍም መንግሰት ድርሻውን ያገኛል፡፡ በኢህአዴግ ሰፈር ያለው ችግር የልማት ባለቤት ህዝብ ይሁን ወይስ መንግሰት የሚለው ነው፡፡ የግል ባለይዞታዎች ከቴሌ ትርፍ ካተረፉ የብር ኖት አይበሉም መልሰው አዋጭ ነው ብለው ባሉት መስመር ኢንቨስት ያደርጉታል፡፡ ምን አልባትም ከመንግሰት በተሻለ አዋጭ መስመር ነው ስራ ላይ የሚያውሉት፡፡ ለዚህ ጉልዕ ምሰሌ በመንግሰት እጅ የሚገኙ የነበሩትን የቢራ ፋብሪካዎች አሁን ለመንግሰት እየከፈሉ ያሉትን ታክስና በኢኮኖሚ ውስጥ እየፈጠሩ ያሉትን መነቃቃት ነው፡፡ እነዚህ ተቋሞች በመንግሰት እጅም እያሉ አትራፊ ነበሩ፤ አሁን ግን የበለጠ አትራፊ ናቸው፡፡
በዋነኝነት የቴሌ በመንግሰት እጅ መቆየት የሚፈለገው ለልማት ካለው ፋይዳ እንዳልሆነ ይገባናል፡፡ በስልጣን ለመቆየት ግን እንዲህ ያለን ህዝቦችን የሚያስተሳሰር ቴክኖሎጂ በግለሰብ እጅ አስገብቶ የነፃነት በር ሆኖ እንዲያገለግል አይፈለግም፡፡ ለሃምሳ ዓመት መግዛት የሚፈልግ ፓርቲ በዚህ ደረጃ ወርዶ ለማፈን ቢሞክር ባህሪው ነው ብሎ መውሰድ ነው፡፡ በልማት ስም በተለይ ለገጠሩ ህዝብ ለማስፋፋት ብለው ሰበብ ከሰጡ በኋላ ግን የቴሌ ገንዘብ ለባቡር መስመር ዝርጋታ እየዋለ ነው ብለው የገጠሩን ህዝብ ለመጠቀሚያ ብቻ እንደሆነ ይፋ አድርገዋል፡፡ የቴሌው የህዝብ ግንኙነት በቅርቡ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አሁን በተያዘው ማስፋፊያ 85 ከመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ ክፍል በኔትወርክ ይሸፈናል ብለዋል፡፡ ይህ ማለት ጠቅላላ ሀገሪቱን ለመሸፈን የቀረው ጥቂት ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አገልግሎቱን
ግርማ ሠይፉ ማሩ
ከመንግሰት በተሸለ ጥራት ለሚሰጡ የግል ድርጅት አስተላልፉ፣ መንግሰት የመሰረተ ልማት ማስፋፊያና ቁጥጥር ላይ ለምን አይገባም
የሚለው መከራከሪያ አሁንም ለፊት ለፊት ጉንጭ አልፋ ጭቅጭቅ እንጂ ይህ ሊሆን የሚችለው በአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ
መቃብር ላይ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ይዘገይ ይሆናል እንጂ ይህ እንደሚሆን ግን ጥርጥር የለውም፡፡ ማለትም አብዮታዊ ዲሞክራሲ
አስተሳሰብ ወደ መቃብር ይወርዳል፡፡
እዚህ ጋ ሊሰመርበት የሚገባው ነገር የግል ባለሀብቱን ስብሰባ እየጠሩ የግሉ ዘርፍ ምትክ የሌለው እንደሆነ እናምናለን፤ ከግል ዘርፉ ጋር ጠብ የለንም የሚል መንግሰት ጠቅላይ ሚኒስትር “መንግሰት ብቻ ነው ይህን ትርፍ ለልማት የሚያውለው” ማለት እንዴት ያለ ተቃርኖ እንደሆነ ነው፡፡ በግለሰቦች (ሲደመሩ ህዝብ የሚሆኑት) እምነት የሌለው መንግሰት፤ የህዝብ ወኪል የሚሆን አይደለም፡፡ በህዝብ ስም ግን ይነግዳል፡፡ መንግሰት ብቻ ነው የሚያለማው የሚለውን ከወሰድን የአሜሪካ መንግሰት ከመከላከያ እና ከተወሰኑ ፓርኮች በስተቀር የመንግሰት የሚባል ነገር የለውም፡፡ በአሜሪካ ልማት የለም በቻይና ነው ያለው እንደማይሉ ተሰፋ አደርጋለሁ፡፡ ብዙ ሰው ቻይና ከአሜሪካ ቀጥሎ ግዙፉ ኢኮኖሚ እያሉ ሲሳሳቱ አሜሪካ ቻይናን 10 ዕጥፍ እንደምትበልጣት የምናውቅ አይመስላቸውም፡፡ ቻይና ከጃፓን በለጠች እንጂ አሜሪካ ጋር አልደረሰችም፡፡ ይህችን እንደ እግረ መንገድ ያዙልኝ፡፡ እርግጥ ነው የቻይና መንግሰት ሀብታም ነው፣ ህዝቡ ግን ድሃ፡፡ ምክንያቱም ፍልስፍናው መንግሰት ብቻ ነው የሚያለማው የሚል እና የኛዎቹም ቅጂያቸው እንደዚያ ስለሆነ ነው፡፡ ሰትራቴጂው ገጠሩን እዚያው ገጠር ለማሰቀረት እቅድ ከሌለ በስተቀር የገጠሩ ህዝብ አሁን የሚፈልገው ስልክ እና መብራት ይዛችሁለት በጫካ ስር መኖር ሳይሆን ከተሜነት ነው፡፡ ወደ ስልኩ እና መሰረተ ልማቱ መምጣት ይኖርበታል፡፡
የታክስ ምጣኔ እና የታክስ መሰረት ማሰፋት
ግብር በማይከፈልበት የቦርድ ክፍያ እና ሌሎች ገቢዎች ለሚደጎም ባለስልጣን ብዙ ግልፅ ያልሆነ ግን ደሞዝተኛውን በከፍተኛ ደረጃ እየጎዳ ያለው ከፍተኛ ታክስ የሚከፈልበት የደሞዝ ጣሪያ አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ አለመሆኑ ነው፡፡ በጋዜጠኞች የቀረበውም ጥያቄ ይህን የሚመለከት እንጂ አጠቃላይ የታክስ ሪፎርም እየተባለ ለረዥም ጊዜ የተያዘ የተሰፋ ፕሮጀክት ምንደረሰ የሚል አይደለም፡፡ ደሞዝተኛውን ደሞዝ ጨመርንልህ ብሎ በግብር ከመቀማት በተግባር የታክስ ምጣኔውን ማስተካከል የዘገየ ብቻ ሳይሆን የዜጎችን የስራ ተነሳሸነት እየገደለ ያለ በምድር ላይ ያለ ሀቅ ነው፡፡ የነዳጅ ዋጋ በዓለም አቀፍ ገበያ ጨመረ ብሎ በየጊዜው የነዳጅ ዋጋ የሚጨምር ፣ ይህንንም ተከትሎ የትራንስፖርት ዋጋ ላይ ጭማሪ የሚያደርግ መንግስት በቀጥታ ከደሞዝተኛ ላይ የደሞዝ መቀነስ እንደሆነ መረዳት አዳጋች አይደለም፡፡ ለኢትዮጵያ ሲቪል ሰራተኞች የመነሻ ደሞዝ ከፍ ማድረግ (ዝቅተኛ የደሞዝ መጠን መወሰን) እና የግብር ማሰከፈያውን የገቢ መጠን ከፍ ማድረግ አፋጣኝ ምላሽ የሚሻ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ዜጎች የሚያገኙትን ገቢ እየተከታተለ የሚቀማቸውን አይፈልጉም፡፡ መንግሰትም ቢሆን፡፡ በታክሰና ግብር ስም እየቀሙ እኔ ለልማት አውለዋለሁ ማለት ከስድብ አይተናነሰም፤ ዜጎችም ሰርተው የሚያገኙትን ገንዘብ ለልማት ለዚያውም ለዘላቂ ልማት ነው የሚያውልቱ፡፡ ከዜጎቹ እየቀማ ዜጎችን በማደኽየት የሚበለፅግ መንግሰት ልማታዊ ነኝ ሊል አይችልም፡፡
ሊስትሮም ሁን ብባል ወረዳም ሂድ ከተባልኩ አደርጋዋለሁ፤
ሊስትሮም ሁን ብባል ወረዳም ሂድ ከተባልኩ የምሄድ ወታደር ነኝ፡፡ ይህ አባባል በኢህአዴግ ሰፈር የግል ነፃነት ስለሌለ ምን ያህል እውቀት እንደሚባክን ነው የሚያሳየው፡፡ ልክ ነው በሚቀጥለው ዙር ወደ ክልል ቢባሉ ሊሄዱ ይችላሉ፡፡ አሁኑ በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ማዕረግ የሚያገለግሉት ቱባ ባለስልጣን ወደ ክልል ብሎም ወደ ዞን ሲላኩ እሺ ብለው መሄዳቸው የዚሁ ማሳያ ነው፡፡ ከክልል ፕሬዝደንትነት ወደ ጠቅላይ ሚኒሰትረ አማካሪነት ተመሳሳይ የምደባ ዝውውር ነው፡፡ ይህ ግን በምንም ምክንያት ተገቢ ነው ብሎ መውሰድ አይቻልም፡፡ ቅዱስ መፅሐፍ ምሳሌ 4፡18 “የጻድቃን መንገድ እንደ ንጋት ብርሃን ነው፤ ሙሉ ቀን እሲከሆን ድረሰም እየጨመረ ይበራል” ይላል፡፡ ምን ነው የኛ መሪዎች ቁልቁል ማየት ፈለጋችሁ፡፡ የሌሎች ሀገር መሪዎች ከመሪነት ሲለቁ ተከታይ ቦታቸው ሊሰትሮ መሆን ወይም የእርሱ ተመጣጣኝ አይደለም፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ አማካሪነት ነው፡፡ ዛሬ ክሊንተን አንድ ሰዓት ንግግር አድርገው የሚያገኙት ገንዘብ ከወረዳ በጀት በስንት እጥፍ እንደሚልቅ ነጋሪ የሚፈልግ አይመስለኝም፡፡ ይህን ብቃት አረጋግጫለሁ ያለ ሰው ወረዳ ለመሄድ አያስብም፡፡ በምደባ የተገኘ ስልጣን ግን በምደባ ሊነሳ ይሚችል ነው፡፡ በምደባ ከሚገኝ ስልጣን ያድነን፡፡ እኔ ግን ከዚህም በላይ የገባኝ፣ የጋራ አመራር አለ ብሎ ከግል ተጠያቂነት ለመሽሽ እንዳይሆን የሚል ፍርሃትም አለኝ፡፡ ሌላው ግን አብዛኛው ሹመኛ ነገ ወረዳ ልወረወር እቻላለሁ በሚል ስጋት ተግቶ በዘረፋ ይሰማራል፡፡ የብቃት ከግምት መውጣትና የምደባ ሹመት የሚያመጣው ጣጣ እጅግ ብዙ ነው፡፡ ለዛሬ ይብቃን ቸር ይግጠመን፡፡
ኢትዮሚድያ – Ethiomedia.com

Image

ብርሃኑ ሃይለስላሴ ይባላል። አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ እያለ ጥናቱን ትቶ በካድሬነት ተግባር የተሰማራ እንደነበር አውቃለሁ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የምንማር የትግራይ ልጆችን እየሰለለ ነበር የሚውለው።

ተመረቀና በህወሓት አባልነቱ መሰረት የትምህርት ዉጤቱ ግምት ዉስጥ ሳይገባ፣ ሳይወዳደር (ሌሎች ብቁ ሰዎች እያሉ) በእምባ አለጀ ወረዳ የጤና ጥበቃ ሐላፊ ተደርጎ በፓርቲ በመሾሙ ዓዲሽሁ ከተማ ገባ። በዓዲሽሁ ከተማ ብዙ ሴቶችን ደፈረ። ህዝብ ጮሆ። ሰሚ የለም። ምክንያቱም ሐላፊ ነው።

ሴቶችን በመድፈር ወንጀል ከመክሰስ ይልቅ ሌሎች ሰራተኞች ያላገኙት የማስተርስ ትምህርት ዕድል ተሰጠው። ሴቶች ስለደፈረ ተሸለመ ማለት ነው። በጦላይ ለስልጠና ተልኮ እዛም ሌላ ሴት ደፈረ። የተደፈረች ሴት የሕግ ከለላ አጥታ ከሱ ጋር እንድትታረቅና ክስ ላትመሰርት ተገደደች።

ከስልጠና በኋላ ህወሓቶች የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል CEO አድርገው ሾሙት። እነሱ ምን ይሳናቸዋል!? በማይጨው ከአንድ ዓመት ባልበለጠ ግዜ ዉስጥ አስራ አራት ሴቶችን ደፈረ፤ ስልጣኑን ተገን በማድረግ። ሴቶች አቤት ይላሉ። ግን ሰሚ የለም። በማይጨው ሰው በመኪና ገጨ። ራሱ ሰው ገጭቶ ሽፌሩ እንደገጨ ለማስመሰልና ከቅጣት ለመዳን ከሽፌሩ ጋር ተዋዋለ። ክስ ተመስርቶበት፣ በፖሊስ ተይዞ በስድስት ሺ ብር ዋስ ተለቀቀ።

ይህን ሁሉ ግፍ ሲፈፅም የማይጨው ኗሪዎችና የሆስፒታሉ ሰራተኞች ቅሬታ አሰሙ። ረበሹ። ተሰበሰቡ። የሆስፒታሉ ሰራተኞች ተሰብሰበው ከፓርቲ አባልነቱ እንዲወገድ ጠየቁ (ምክንያቱም የገዢው ፓርቲ አባል በመሆኑ ስልጣኑ ተገን አድርጎ ነው ግፍ እየፈፀመ ያለው ከሚል እሳቤ)። ከስራ (ከሐላፊነቱ) ታግዶ በፖሊስ እንዲያዝ ወሰኑ። ቢሮው ታሽጎ ሁለቴ ቁልፍ ሰብሮ መግባቱ ተረጋገጠ። ማንም አልጠየቀውም።

አቶ ብርሃኑ ሃይለስላሴ በሰራተኞቹ ስብሰባ ቀርቦ ሁሉም የተጠቀሱት ወንጀሎች መፈፀሙ አምኖ ይቅርታ ጠየቀ። በተበዳዮቹና ሰራተኞቹ ግፊት በፖሊስ እንዲታሰር ተደረገ። ህዝቡ ተረጋጋ። እኛም “ኮርማው ታሰረ!” ብለን በፌስቡክ ፃፍን። ህወሓቶች ለምን አስራ ስምንት ሴት እስኪደፍር ድረስ ዝም አሉት? ሕግ ለካድሬዎችስ አይሰራም ወይ? ብለን ጠየቅን። የህወሓቶች አድሎአዊ አሰራር ወቀስን። መታሰሩ ግን ጥሩ መሆኑ ጠቆምን።

አቶ ብርሃኑ በፖሊስ ከታሰረ ከሁለት ቀናት በኋላ መለቀቁ ሰማሁ። መለቀቁን አስመልክቼ በፌስቡክ ፃፍኩ። መለቀቁ ግን በሌላ አካል አልተረጋገጠም ነበር።

አሁን ከአስራ ስምንት ሴቶች በላይ የደፈረ ባለስልጣን ምን ቢቀጣ ጥሩ ነው!? አሁን በደረሰኝ መረጃ መሰረት አቶ ብርሃኑ አልታሰረም። ወደ ሌላ የስራ ቦታ ተዛወረ እንጂ። ህወሓቶች አንድ ባለስልጣን ወንጀል ከሰራ ባለስልጣኑ ከመቅጣት ይልቅ ወደ ሌላ የስራ ሐላፊነት ይቀይሩታል። ቅጣት ግን የለም። ሽልማት እንጂ።

አሁን አቶ ብርሃኑ ከዞን (ከማይጨው) ወደ ክልል (መቐለ) የስልጣን እርከን አድጎ በመቐለ የትግራይ ክልል የጤና ቢሮ የHMIS ዲፓርትመንት expert ሁኖ በሙሉ ደሞዝና የተሻለ የሐላፊነት ደረጃ እየሰራ ይገኛል። ይህን ጉዳይ የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል ሐላፊዎች አረጋግጠውታል። ለምን የሚል ጥያቄም አስነስተዋል። አሁን በማይጨው ሆስፒታል ሰራተኞች ጥሩ ስሜት የለም።

አሁን እንደሰማነው ግን ከእሰር የተፈታው በህወሓቶች ነው። በክልል ጤና ቢሮ እንዲሰራ ትእዛዝ ያስተላለፈውም አቶ ሃይሉ አስፈሃ የተባለ የደቡባዊ ዞን ዋና አስተዳድሪና የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል የቦርድ ሰብሳቢ ነው። የሆስፒታሉ ሰራተኞች ይሁኑ የቦርዱ አባላት ሳይሰበሰቡና ምንም መረጃ ሳይኖራቸው አቶ ሃይሉ አስፈሃ (የቦርዱ ሰብሳቢ) ግን የቦርዱ ዉሳኔ እንደሆነ አድርጎ ደብዳቤ በመፃፍ በክልል ጤና ቢሮ እንዲቀጠር ማድረጉ ለማረጋገጥ ተችሏል።

ባሁኑ ሰዓት በማይጨው ከተማ ኗሪዎችና ለምለም ካርል ሆስፒታል ሰራተኞች በከባድ ቀውስ ዉስጥ እንደሚገኙ ለማወቅ ችያለሁ። የማይጨው ህዝብ በዋና አስተዳዳሪው አቶ ሃይሉ አስፈሃ ከፍተኛ ቅሬታ እያነሳ ሲሆን ህወሓቶች ለህዝብ ያላቸው ንቀት እያሳዩን ነው በሚል የተቃውሞ መንፈስ እንዳለ ከማይጨው ኗሪዎች የደረሰኝ መረጃ ያመለክታል።

አይ ህወሓቶች መቼ ነው ለህዝብ ደህንነት የምትቆሙ? በትግራይ የሚፈፀሙ አስተዳደራዊ በደሎች ቢጋለጡኮ ስንት ጉድ በሰማን ነበር! ይህን ጉዳይ እስከመቼ እንችለዋለን?!

በህወሓት እምነት የለኝም። ከዚህ በላይ ምን ሊያደርገን ይችላል!? እናንተስ?

It is so!!! ABRHA DESTA

በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል በተደረገው የድንበር ጉዳይ ስምምነት መሰረት ኢትዮጵያ ወደግዛቷ 62.6 ኪሎ ሜትር ዘልቆ የሚገባ እና በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የሚያፈናቅለውን የመሬት ርክክብ በምስጢር መፈጸሟን ተከትሎ በዚሁ ሱዳን በምትረከበው ድንበር አከባቢ የመሬት ጥያቄ የሚይነሱ የሚያምጹ እና የሚሸፍቱ ሊኖሩ ይችላሉ በሚል ወያኔ የሱዳን ሰራዊት እና የራሱ ምልምል የሆኑ ትውልዳቸው ሱዳን የሆነ ኢትዮጵይውያንን አሰልጥኖ ህገወጦችን መቆጣጠር በሚል ሽፋን የድንበር አከባቢ ተወላጆችን ለማስመታት በዝግጅት ላይ መሆኑ ታውቋል::

ይህ ይቋቋማል የተባለው የጋራ የጦር ሰራዊት ህገወጥ ብሎ የፈረጃቸውን እና የመሬት ጥያቄ ሊያነሱ ይችላሉ ተብለው የሚገመቱትን የአማራ ገበሬዎች ለመምታት የታቀደ እና እንዲሁም ይህንን ተከትሎ የተቃዋሚ ድርጅቶች አማጺያን ሰርገው ይገባሉ በሚል ስጋት የመከላከያ ሚኒስትሩ ሲራጅ ፈርጌሳን ወያኔ ወደ ካርቱም ልኮ ሚኒስትሩ ሳምንት ካርቱም ሰንብተው ወደ ሃገር ቤት መጥተዋል::

በሰሜን ጎንደር በምእራብ ጎጃም በቤንሻንጉል እና በጋምቤላ አከባቢዎች ወያኔ ፋታ የማይሰጡ የለውጥ ጥያቄ ያላቸው ታጣቂ አማጽያን ጦር ወድረው እየተኮሱበት መሆኑን ያማረረው ኢሕኣዴግ የሱዳንን መንግስት በመማጸን የጋራ የጦር ሰራዊት በማቋቋም በጀቱን ኢሕኣዴግ ከህዝብ ቀረጥ ከሚከፍልበት ገንዘብ የሚሸፍን መሆኑ ተረጋግጧል::ምንሊክ ሳልሳዊ

© Masresha Mammo
የኢትዮጵያ ፖለቲካ የሞራል መሠረት እና ብቃት በሌላቸው ፖለቲከኞች እጅ ከወደቀ ሰንብቷል። ይህ የሰነበተ እውነታ በአሁን ሰዓት ከዝቅጠትም በታች እየኾነ ነው። ለኢትዮጵያ የሚያዋጣት ብሔርን መሠረት ያደረገ ፖለቲካዊ ርዕዮት ነው የሚለው የፖሊቲካል ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ሁሉን አቀፍ ፍትህ የተንሰራፋበት ቢኾን ምናልባት አዋጪ ሊኾን ይችላል የሚል ግምት ማስቀመጥ ይቻል ነበር። ነገር ገን ስትራቴጂው ወረቀት ላይ ሌላ መልክ የያዘ፤ ምድር ላይ ደሞ ሌላ ትርክት የዋጠው ነው። ከጅምሩ ፍትሃዊነቱ አጠራጣሪ ስለኾነ ስትራቴጂው ለማፋጀት ያለመና እርስ በርስ በጥርጣሬ ከመተያየት የማያመልጡ የብሄር ፖለቲከኞችን እየፈለፈለ ይገኛል። ለዚህም ነው ከሁለት ዐሥርተ ዓመታት በፊት “በትምክህት” ፍረጃ የተጸነሰው ሕዝብን የማቃለል ጅምር ወደ ለሃጭ ተዋስዖ ያደገው።

የብአዴን ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አለምነው መኮንን ይህን የለሃጭ ተዋስዖ ከየት አመጡት? የሚለው ጥያቄ በእኔ እምነት ወሳኝ ጥያቄ ነው። ብዙዎች እንደሚያምኑት ብአዴን እንደ ፓርቲ የራሱ የኾነ ነጻነት እና እምነት ያለው ፓርቲ አይደለም፤ አሻንጉሊት እና አስፈጻሚ፤ ከሕወሃት የሚወርድለትን ትዕዛዝ እና ፖለቲካዊ ትንተና ለማስተላለፍ የሚያገልግል “ትቦ/ቧንቧ ፓርቲ” ነው። ከአራቱ የኢሕአዴግ ፓርቲዎች ውስጥ ራሱን ሥልጣን እንደሚጋራና 22 ሚልዮን ሕዝብ እንደሚወክል ድርጅት ፖለቲካዊ ስሌት ውስጥ አስገብቶ የሚንቀሳቀስ ፓርቲም አይደለም። “የአማራውን” ሕዝብ ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችል ምንም ዐይነት ተነሳሽነትም የለውም። ይህን እውነታ በግልጽ ለመረዳት የፓርቲውን ቁልፍ ሰዎች ማንነት ማየት ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ። አንድ የብሔር ፓርቲ የአባልነት መመዘኛ መስፈርቱ ምንድነው? የሚለውን ጥያቄ ቀድመን እናንሳ። በደም እና በዘር ከዚያ ብሔር የተገኘ ሰው ብቻ ነው የፓርቲው አባል መኾን ያለበት? ወይስ በምርጫም የዚያ ብሔር አባል ነኝ ማለትን ያካትታል?

የሚያካትት ከኾነ በብሔር የመደራጀት ትርጉም ለምን ያስፈልጋል የሚለውን ጥያቄ ማንሳታችን አይቀርም። ይህን ጉዳይ ማንሳት የፈለግኹት የመንግሥት ቁልፍ ሰው ናቸው ተብለው የሚነግርላቸውን አቶ በረከትን እንደምሳሌ ለመመልከት ነው። አቶ በረከት በደም ከአማራው ጋራ የሚያስተሳስራቸው አንዳችም ነገር የለም። ነገር ግን የአማራው ጉዳይ የእኔ ነው ብሎ በተቀመጠው ፓርቲ ላይ ቁልፍ ቦታ አላቸው። የብአዴን አመራሮችም ኾኑ አባላት አቶ በረከት ከዚህ ፓርቲ ራሳቸውን እንዲያወጡ መጠየቅ አለባቸው፤ ቡግና ውስጥ ተወልዶ ማደግ አማራነትን ያቀዳጃልና እኔም አማራ ነኝ የሚል አቋም ካላቸው፤ ቀድመህ ለተገኘህበት የብሔር ማንነት ቅድሚያ ስጥ ከሚለው የራሳቸውና የተከታይ ካድሬዎቻቸው ትንተና ጋራ ስለሚጋጭ የሚያዋጣ አካሄድ አይኾንም። እንደ በረከት ዐይነት “የአማራነት ልብስን ቀደው ያሰፉ” ሰዎች ለአማራው ሕዝብ ቆመናል ብለው ከሚያስቡ ሰዎች ጋራ በአንድ ጠረጴዛ ላይ መቀመጣቸው መዘዙ ብዙ ነው። በዋነኛነት ሌሎችን ነጻነት ያሳጣቸዋል። ነጻነት የሌለው ሰው ደግሞ ከራሱ የሚናገረው ነገር የለውም።

አቶ በረከት ከጫካ ጀምረው የሕወሓት ዋነኛ ሐሳብ አስተግባሪ ናቸው። አማራ ትምክህተኛ እና ነፍጠኛ ነው የሚል የፖለቲካ መሣርያ ይዘው መሥራት የጀመሩት ዛሬ አይደለም። አማራው እንደ ሕዝብ ትምክህት አለበት ወይ የሚለው ሐሳብ በራሱ ሕዝብን በአንድ ቅርጫት ውስጥ አስገብቶ እንደመፍረድ ስለሚቆጠር ሐልዮቱ በራሱ ወኃ የሚያነሳ ጭብጥ የለውም። የአማራውን ልሂቅ ስህተት እና ተግባር ከሌላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋራ ጭቆናን ሲካፈል ለኖረ ሕዝብ ማሸከምም የወጣለት ኢ-ፍትሃዊነት ነው። የትኛውም አማራ፤ የትኛውም ትግሬ፣ የትኛውም ኦሮሞ፣ የትኛውም ጉራጌ፣ የትኛውም ወላይታ . . .እና ሌሎችም ብሔሮች የጨቋኝ አገዛዝ ሰለባዎች ነበሩ፤ እንደ ሕዝብ። አሁንም ናቸው። አማራ እንደ ሕዝብ የተለየ ያገኘው ጥቅም አለ ብዬ አላስብም። ስለዚህ አማራውም እንደ ሕዝብ በብሔር መብቱን ያስጠብቅ የሚል መነሻ ይዘን ከመጣን ስድብን ተሸክሞ የሚዘልቅበት ምንም ዐይነት ምድራዊ ምክንያት ሊኖር አይችልም።

የህወሓት ከፍተኛ ባለሥልጣናት አማራውን ወክለናል ብለው በሚንቀሳቀሱ አመራሮች ላይ ለምን “ትምክህተኛ”፣ “ነፍጠኛ” እና “ለሃጫም” የሚሉ ቃላቶችን በአፋቸው ላይ ማስቀመጥ መረጡ? በኦሮሞው ላይ “ጠባብ” እና “ሁሉም ሲፋቅ ኦነግ ነው” የሚለውን ፍረጃ እና ስድብ ማሸከምስ ፈለጉ? ይህን ፍረጃ እና ስድብ የመረጡበት ምክንያት አንድና አንድ ብቻ ነው። የሁለቱ ብሔሮች ጥንካሬ የሥልጣን መሠረታቸውን ስለሚያናጋ ነው። ራሳቸው ቀይደው ባመጡት የብሔር ፖለቲካ አደረጃጀት ኦሮሞው እና አማራው ባላቸው የሕዝብ ብዛት ብቻ የሥልጣን ተቀናቃኝ በመኾን ወደፊት የሥልጣን ርካብ ላይ እንደ ሕወሓት ያለው ድርጅት እንዳይወጣ እንደሚያደርገው ጠንቅቀው ያውቃሉ። ስለዚህም “እኔ ትምክህተኛም፤ ጠባብም አይደለሁም” የሚለውን ፍረጃ መልስ እስኪሰጡበት ድረስ ሥልጣናቸውን ማራዘም ይፈልጋሉ። ሕወሃት ለሌሎቹ የኢትዮጵያ ብሔሮች ቀርቶ ሕዝባዊ መሠረት አለኝ ለሚለው የትግራይ ማኅበረሰብም የማይገደው መኾኑን በተደጋጋሚ አሳይቷል። (ለዚህ የአብርሃ ደስታን ሪፖርቶች መከታተል ብቻ በቂ ነው)።

ብዙ የነቁ የትግራይ ልጆች እና ራሳቸውን ከአረና ጎን አሰልፈው የሕወሃትን አምባገነናዊ አስተዳደር ለሚታገሉ ሰዎች የሚያወጣላቸው ስም አማራውን እና ኦሮሞውን ከፈረጁበት ጋራ ተመሳሳይ ነው። አሁንም አዲሱ “የትምክህት ለሃጭ” ተዋስዖ በገዛ ልጁ አባቱን ማሰደብ ዐይነት ነው። ይህ አዲስ ነገር አይደለም። የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ይህንኑ ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽመዋል። ይህ ሕዝብን የማቃለል እና በእሳት ላይ ቤንዚን የማርከፍከፍ ተግባር ተጸንሶ የሚያድገው በሕውሓት ሴል ውስጥ አይደለም ብሎ ማንም አይጠረጥርም።

በ97 ምርጫ ገዢው ፓርቲ ከተቃዋሚ ፓርቲ በኩል ያለው ጫና እየበረታበት ሲመጣ እና በፖሊሲ ክርክሮች ላይ ሕዝቡ የበለጠ ድምጹን ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ሊሰጥ ወደሚችልበት ኹኔታ ባዘነበለበት ወቀት “ኢንተርሃምዌይ” የምትለዋን ቃል ከአለቃቸው ተቀብለው በቴሌቪዥን መስኮት መጥተው የነገሩን አማራውን እወክላለሁ ብለው የተቀመጡት አቶ አዲሱ ለገሰ ነበሩ። ከራሱ አፍልቆ ያመነበትን ነገር በራሱ ቋንቋ የሚናገር አንድም ባለሥልጣን እንደሌለን እናውቃለን። አቶ መለስ ቃላቶችን ይፈበርካሉ፤ እነዚያን የተፈበረኩ ቃላት በዙሪያቸው ኅሊና እና ሆዳቸውን የሸጡ ባለሥልጣናት እንደ ዐየር ባየር ነጋዴ አውጥተው እንደ በቀቀን ሲጮኹብን ይውላሉ።

እጅግ በጣም አስገራሚው ነገር ኢሕአዴግ ውስጥ ካሉት አራት ድርጅቶች መካከል በአመራር ደረጃ ለወከሉት ሕዝብ ባለመቆርቆር ብአዴኖችን የሚተካከላቸው አለመገኘቱ ነው። በታምራት ላይኔ ተጀምሮ፣ በአዲሱ ለገሰ ተባብሶ፣ በአለምነው መኮንን የዝቅጠት ደረጃ ላይ ደርሷል። ምንም እንኳ “የዘር ምርጥ፤ ወይም ንጹህ ዘር” የሚባል ጽንሰ ሐሳብ በዚህ ዓለም ላይ ባይኖርም፤ (አለ ብለው የሚያስቡ ካሉ፤ እንደ ሂትለር ዐይነት በሽታ የተጠናወጣቸው ይመስለኛል) አንዳንዶች የእነሱን ዘር ከሌላው ዘር የተለየ እና የተሻለ አድርገው ለማሳየት ሲታትሩ እየተመለከትን ነው። እያንዳንዱ የሰው ልጅ ሲፈጠር እኩል ነው የሚለውን ዋናና መሠረታዊ ጉዳይ ኾነ ብለው ለመሸሽ ፖለቲካዊ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ “ማንነት እንዲህ ነው፤ እንዲያ ነው” በሚል ጉንጭ አልፋ ክርክር ውስጥ የሚገቡ ሰዎችም ሞልተዋል። እነዚህ በፖሊቲካ መጫዎች ሜዳው ታስቦ እና ተሰልቶ ከተቀመጠላቸው ተዋስዖ ውጪ አዲስ ተዋስዖ መፍጠር ያቃታቸው ናቸው። ቀጣይቱ ኢትዮጵያ አዲስ ተዋስዖ ያስፈልጋታል። ሁሉም የሰው ልጆች በመጀመርያ እኩል ናቸው በሚል መሠረታዊ ኀልዮት ላይ የሚያጠነጥን ተዋስዖ።

የለሃጭ ተዋስዖው በሁለት ወገን ራሳቸውን የቀየዱ ልጋጋም ተፋላሚዎችን እያሳየን ነው። “ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል” ወደሚል መፈክረኛነት መሻገር አርቆ አሳቢነትን የሚያሳይ እንዳልኾነ ግልጽ ነው። ምክንያታዊ ከኾኑ ምልከታዎች ወጥተን የስድብ ጅራፍ የምናጮህ ትውልዶች መኾናችንም አሳዛኝ እውነታችን ኾኗል። አማራው እንደ ሕዝብ እየተሰደበ ነው የሚለው ነገር የሚያስቆጣን እና የሚያንገበግበን ከአማራ ስለተወለድን ብቻ ከኾነ ፍትሃዊ የመኾን ዕድላችን ይመነምናል። ይህ ማለት ግን መሰደብን አሜን ብላችሁ ተቀበሉ እና እለፉት ከሚል እሳቤ ጋራ ፈጽሞ አይገናኝም። ግለሰቦችም ኾኑ ብሔሮች በማንኛውም ኹኔታ መሰደባቸውን መቃወም እና መታገል ነው ዋናው እና ትልቁ ቁም ነገር።
በሌላ በኩል ሌላው ብሔር ሲሰደብ ወገባቸውን ታጥቀው የሚመጡ ሰዎች አማራውም እንደ ሕዝብ ሊሰደብ አይገባውም ብለው ከጎኑ ካልቆሙ፤ ለብሔር እንቆረቆራለን የሚሉት ጊዜያዊ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ትርፋቸውን ለማስጠበቅ ብቻ እንደኾነ ያሳብቅባቸዋል። ይህ ደግሞ እንደ አገርም ኾነ እንደ ማሕበረሰብ ዘላቂ የኾን ትርፍ የምናካብትበት ጉዳይ አይኾንም።

ለብሔር/ለጎሳ ፖለቲካ ቅድሚያ ሰጥተው የክርክር ሰይፋቸውን የሚመዙ ሰዎች አሁን አማራ በሚባለው ብሔር ላይ የተቃጣውን ስድብ ሲቃወሙት ካላየን፤ የሚከተሉት ፖለቲካዊ ርዕዮት ሚዛን የሚደፋ ነው ብለን እንድናስብ አያደርጉንም።

በእኔ እምነት አቶ አለምነው መኮንን የፈጸሙት ነገር ወንጀል ነው። ያውም ትልቅ ወንጀል። ጉዳዩ በግምገማ ወይም ከሥራ ኀላፊነታቸው ዝቅ በማድረግ ብቻ የሚታለፍም አይደለም። የሚመራውን ሕዝብ በዚህ ደረጃ አሳንሶ እና አዋርዶ የሚመለከት መሪ ፓርቲውንም ኾነ አገሩን አይጠቅምም። የፌዴራል መንግሥቱ የክልል መንግሥታት እና ባለ ሥልጣናት የህዝብን ክብር እና ስም የሚያጎድፍ ተግባር ሲፈጽሙ ነገሩን የሚዳኝበት የራሱ የኾነ ሕገ መንግሥታዊ ማዕቀፍ አለው። በዚህ ጉዳይ ላይ መንግሥት ርምጃ የመውሰድ የሞራል ብቃትም ኾነ መሠረት የለውም የሚል መከራከርያ ሊነሳ እንደሚችል እገምታለሁ። ይህ መከራከርያ እና ግምት ትክክል ነው ብዬም አምናለሁ። ይህ ዐይነቱ በሕዝብ ላይ ቁጣ ሊያስነሳ የሚችል ድርጊት ከወዲሁ በራሱ በፌዴራል መንግሥቱ መልስ የማያገኝ ከኾነ፤ ራሱን በጊዜ ሂደት ከስሩ መንግሎ ሊጥለው እንደማይችል ምንም ማረጋገጫ አይሰጠንም። ይህ ሐሳብ ራሳቸውን በተቃዋሚ ጎራ ላሰለፉ ዜጎች ‘የዋህና የኢትዮጵያን መንግሥት ተፈጥሯዊ ማንነት ካለማወቅ የመነጨ’ ሊመስላቸው ይችላል። ለጊዜው መልሴ ይምሰላችው ግድ የለም የሚል ይኾናል። ነገር ግን በበሰበሰ አሠራሩም ቢኾን ይህን ጉዳይ ችላ ማለት አያዋጣውም ባይ ነኝ። ባለሥልጣናቴ ሙስና ሲሠሩ አገኘኋቸው ብሎ ዘብጥያ ካወረደ፤ አቶ አለምነህን የማያወርድበት ምንም ምክንያት ሊኖር አይችልም ከሚል መነሻም ነው።

በመጨረሻ፦ የአቶ አለምነው ንግግር ማንንም ሰው የኾነ ሰው ሁሉ ምን ያህል ሊያስቆጣ እንደሚችል ለማሳየት ንግግሩን በሌሎች ብሔሮች ገልብጬ ማየት ፈለግሁ። ይህን ማድረግ የፈለግኹት ለብሔር ማንነት ቅድሚያ የሚሰጡ ሰዎች ዝምታ ምን ያህል አግባብ እንዳልነበረ ለማሳየት ነው።

አቶ አለምነው እንዲህ ነበር ያሉት። “አማራው በባዶ እግሩ እየሄደ፤ ነገሩ መርዝ ነው፤ ይህንን የትምክህት ለሃጩን ካላራገፈ በአንድነት አብሮ መኖር አይችልም!”

ይህንኑ ንግግር የሕወሃት ምክትል ፕሬዝዳንት እንዲህ ብለው አቀረቡት ብለን እናስብ “ትግሬ በሰቆጣ እየሄደ፤ ነገሩ መርዝ ነው፤ የእብሪት ለሃጩን ካላራገፈ በአንድነት አብሮ መኖር አይችልም!”

እንደገና ይህንኑ ንግግር የኦህዴዱ ምክትል ፕሬዝዳንት ሲያቀርቡት “ኦሮሞ በቦት ጫማ እየሄደ ነገሩ መርዝ ነው፤ የመገንጠል ለሃጩን ካላራገፈ በአንድነት አብሮ መኖር አይችልም!” ቢሉ ምላሾቻችን ምንድን ነው የሚኾኑት? የለሃጭ ተዋስዖ ምናልባትም ልጋግ ኾኖ ሁላችንንም ጠራርጎ እንዳያጠፋን ያሰጋል። ሁላችንም ከጊዜያዊ ጥቅማችን በላይ ለሰው ልጆች እኩልነት እኩል እንቁም።

Image

………………..ቴወድሮስ ከጎንደርና ከአሁኑ አማራ ይልቅ የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ከዚያም አልፎ እየሩሳሌም ነጻ ለማውጣት እቅድ እንደነበረው ይነገራል፡፡አጼ ዮሃንስም እራሱን የትግራይ ሳይሆን የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ነበር፡፡ አሉላ አባነጋ ቀይ ባህር ድረስ ይዋትት የነበረው ለተንቤን አሊያም ለትግራይ አልነበረም፡፡

አጤ ምኒልክ የአንኮበር ወይንም የሸዋ ንጉስ ብቻ አልነበሩም፡፡ ምኒልክና ጀኔራሎቹ አድዋ ድረስ የዘመቱት የአሁኑ ዘመን መሪዎች እንደሚሉት ‹‹ነፍጠኛውን›› ብቻ ወክለው አልነበረም፡፡ ንጉስ ጦና እና ሌሎችም የትግራይን ተራራዎች የወጡ የወረዱት ለእናት ሃገራቸው ኢትዮጵያ ነው።

እንደ በላይ ዘለቀ ያሉ ጀግና የኢትዮጵያ አርበኞች በአምስት አመቱ የትግል ወቅት የጣሊያን ፋሺስትን የተዋጉት ተጋድሎ ያደረጉት ለኢትዮጵያ ሃገራቸው ነው ። በደርግ ዘመን በሶማሊያ እና በኤርትራ ተራሮች ወንበደዎችን የተዋጉት ወታደሮች የእናት ሃገራቸው አንድነት …. በባድመ የተሰዉት ወጣት ወገኖቻችን የእናት አገራቸው አንድነት አነሳስቷቸው ነው። ምንሊክ ሳልሳዊ

Image

በሕወሓት የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ/ ማዕከላዊ ኮሚቴ የድርጅቱን ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበር ተመደበ።

በዚሁ መሰረት ምክትል ሊቀመንበር የነበሩት አቶ ሙክታር ከድር የድርጅቱ ሊቀመንበር ሆነው ተመድበዋል። የድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽህፈት ቤት ኃላፊ የነበሩት ወይዘሮ አስቴር ማሞ ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር ሆነው ተመድበዋል።
የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ/ ማዕከላዊ ኮሚቴ ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበር በሕወሓት የተመደቡት ሕወሓት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ነው።ተመዳቢዎቹ የተሰጣቸውን ተልዕኮ በብቃት የሚወጡ መሆናቸው ታምኖባቸዋል።

በሕወሓት በወረደው ትእዛዝ የኦሕደድ ማዕከላዊ ኮሚቴው የተባለው ምድብ በቅርቡ ባካሄደው ስብሰባ የድርጅቱ ሊቀመንበር የነበሩት የሕክምና ውጪያቸው ከክልሉ በጀት እኩል ስለሆነ ባለመፈለጋቸው አቶ አለማየሁ አቶምሳ በህመም ምክንያት ተብሎ ከስልጣናቸው የተሰናበቱ ሲሆን በቦታው ላይ ከተመደቡ ጀምሮ ምንም አይነት ስራ አልሰሩም ሲል ሕወሓት አማሯል።

Image

(ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)
ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራ በረዳትነት የሚያበረውን ቦይንግ 767 አውሮፕላን አቅጣጫ ቀይሮ ስዊዘርላንድ የፖለቲካ ጥገኝነት በመጠየቅ ካሳረፈ ወዲህ የዓለም አቀፍ የብዙኃን መገናኛውን ትኩረት ይዞ ቆይቷል፡፡ ከዚህ ድርጊት በኋላም በሁለቱም ጎራ ያሉ አካላት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራን በተመለከተ የተለያየ መላምት ትችትና ነቀፋ ሲሰነዝሩበትና ሲሰናዘሩበት ሰንብተዋል፡፡ የሕዝብ ወገን የሆነው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራን ጀግና ነው አርበኛ ነው ሲለው “መንግሥት” እና ደጋፊዎቹ ደግሞ ከሀዲ ነው ብለውታል፡፡

እነኝህ ሁለቱም አካላት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራን በየበኩላቸው ያሉትን ለመሆኑ የየራሳቸውን ማስረጃ የሚሏቸውን ነገሮች በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ የሕዝብ ወገን የሆነው ክፍል ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ጀግና ነው የሚሉበትን ምክንያት ሲጠቅሱ በአገዛዙ ተማሮ የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቁን፣ ይሄንን ድርጊት ከመፈጸሙ በፊትም ለወያኔ ባለመመቸቱ አሜን ወዴት ባለማለቱ እኅቱ በፌስ ቡክ (በመጽሐፈ ገጽ) በሰጠችው ገለጻ መሠረት ስልኬን ጠልፈውብኛል ይል እንደነበር፣ “መንግሥት” በተለያየ ዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች እየተከሰሰ እንዳለው የተለያዩ ግለሰቦችን በኮምፒውተራቸው (በመቀምራቸው) መሰለያ በመጫን እየሰለለ እንደሆነ እንደሚነገረው ሁሉ ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅንንም የግል ኮምፒውተሩን (መቀምሩን) ካሜራ (በመቅረጸ ምስል) በመጠቀም እያንዳንዱን እንቅስቃሴየን ይከታተሉኛል ይል እንደነበር ኮንፒውተሩን (መቀምሩን) ሲጠቀም ካሜራውን (መቅረጸ ምስሉን) ለመሸፈን ይገደድ እንደነበር፣ መኖሪያ ቤቱንም በሌለሁበት እየገቡ ይፈትሹብኛል ይል እንደነበር፣ የሚያስፈራሩት አካላት እንደነበሩ፣ አልፎም ለቤተሰቦቹ እንደሚሠጋ ባጠቃላይ ደኅንነቱ በሚያሳዝን ሁኔታ አደጋ ላይ የወደቀ እንደነበር፣ ይህ ሁሉ ውክቢያና ማስፈራሪያ እየደረሰበትም ለእነሱ ቡድናዊ የፖለቲካ (እምነተ አሥተዳደር) ፍላጎት ባለመንበርከኩ ባለማደሩ ባለመገዛቱ እንደነበር ይህ ሁኔታ ደግሞ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ችግር መሆኑንና አዲስ ነገር አለመሆኑን በሁሉም ዜጎች ላይ እንደሚደርስ አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው የጋራ ችግር መሆኑን ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ግን እንደ ብዙዎቻችን ሁሉ በእነዚህ ግፎች ሁሉ ተንበርክኮ ባለመሸነፉና አሻፈረኝ ብሎ እራሱን ነጻ በማውጣቱ ለዚህ ለደረሰበት ሰላም ለሚነሳ ውክቢያ እጅ አለመስጠቱን በመጥቀስ ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ጀግና እንደሆነ ያረጋግጣሉ፡፡

“መንግሥት” እና ደጋፊዎቹ ደግሞ ምንም እንኳን እስከአሁን ከቦታው በተገኘው መረጃ መሠረት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን የፖለቲካ ጥገኝነት እንዳቀረበ በግልጽ የታወቀ ጉዳይ ሆኖ ያለ ጉዳይ ቢሆንም በማኅበራዊው የብዙኃን መገናኛው የ“መንግሥት” ደጋፊዎች የሆኑቱ የረዳት አብራሪውን የኃይለ መድኅንን ጉዳይ ኢሳትን በመሳሰሉ የብዙኃን መገናኛዎች ፖለቲካዊ ገጽታ ተሰጥቶት በማየታቸው ስሕተት መሆኑን በመኮነን ሲናገሩ ተስተውለዋል፡፡ ማስተዋል ካለመቻላቸው ይሁን የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቅ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ካለማወቃቸው ሊገባኝ አልቻለም፡፡

ጥቂቶት የመንግሥት ደጋፊዎች እና “መንግሥት” ግን ይህ ጉዳይ ምን ማለት እንደሆነ በሚገባ ገብቷቸዋል፡፡ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድም የሠጉት ትርጉም እንዳይወሰድና ስማቸው አሁን ካለበት ደረጃ ይብስ እንዳይጠፋ ያደረጉ መስሏቸው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ይህንን እርምጃ በወሰደበት ወቅት በደኅና በትክክለኛ (normal) የአእምሮ ጤና ላይ እንዳልነበረና ሱሰኛም እንደሆነ በዚህም ምክንያት ድርጊቱን እንደፈጸመ በማስረዳት ለመከላከል እየሞከሩ ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ድርጊታቸው ከድጡ ወደ ማጡ መሆኑን አልተረዱም አልተገነዘቡም፡፡ ድርጊታቸው ፈጽሞ ኃላፊነት የጎደለውና አርቆ ማሰብ የተሳነው፣ አየር መንገዱንም ለከፍተኛ ኪሳራ የሚዳርግ የደነቆረ ማስተባበያ ነው፡፡ ምክንያቱም ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን እንዲህ እንዳሉት ዓይነት ሱሰኛና ሥራውን በትክክል ለመሥራት በማያስችል የመንፈስ ጭንቀትም ሆነ የሥነ ልቡና መታወክ እንዳለበት እየታወቀ ሥራ ላይ በማሠማራት በመቶዎች የሚቆጠሩ ደንበኞቹን ደኅንነት ለአደጋ አጋልጧል የሚል ትርጉም እንደሚያሰጠውና አየር መንገዱ ለደንበኞቹ ደኅንነት የማያስብ የማይገደው የማይጠነቀቅ ኃላፊነት የማይሰማው እንደሆነ ተቆጥሮ ለዘመናት በብዙ ድካም የገነባውን መልካም ስም እንደሚያጠፋው ደንበኞቹንም እንዲያጣ እንደሚያደርገው ያልተረዱና መረዳት የማይችሉ ሰዎች የደነቆረ አርቆ ማሰብ የተሳነው ስም ማጥፋት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሥራየ ብለው ይህንን ስም ማጥፋት ያደረጉትና እያደረጉም ያሉት ደናቁርት አየር መንገዱ ለሚደርስበት ጉዳትና ኪሳራ ኃላፊነቱን የሚወስዱ ይሆናሉ፡፡

በሌላ በኩል በእርግጥም እንደተባለው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን የአውሮፕላኑን አቅጣጫ መቀየር ሳያስፈልገው በራሱ በግሉ በፈለገው ሀገር ላይ በሔደበት ጥገኝነት ጠይቆ መቅረት የሚችል ሰው ነበር፡፡ እንደኔ ግምት ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን ይህንን ያደረገበት ምክንያት ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉት፡፡ የአውሮፕላኑን አቅጣጫ ከሮም ወደ ስዊዘርላንድ ማድረጉና ጥገኝነቱን እዚያ መጠየቁ ሲጠይቅም አውሮፕላኑን መያዙ መውሰዱ ምክንያቱ አንደኛው ሽንት ቤት ሲገባ የቆለፈበት ዋናው አብራሪ ጣሊያናዊ በመሆኑ ለሚያቀርበው የፖለቲካ ጥገኝነት በቂም ምክንያት እንቅፋት እንዳይሆነው በመሥጋቱ ሲሆን ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን በሄደበት ቀርቶ ብቻውን መጠየቅ ሲችል ይሄንን ያላገረገበት ምክንያት ጉዳዩ የሱ የግሉ ጉዳይ ሆኖ እንዲቀር ስላልፈለገ፣ ይህ እሱን ያሰቀቀውና ያንገላታው ችግር የሱ ችግር ብቻ አይደለምና አውሮፕላኑን በመውሰድ የኢትዮጵያን ሕዝብ አቤቱታ በአደባባይ አጉልቶ በማሰማት እንዲያቀርብ አድርጎታል፡፡

ይህ ሰው እንደሌሎቻችን ሁሉ ሆዳም ቢሆን ኖሮ የያዘው የሙያና የኑሮ ደረጃ አይደለም በኢትዮጵያ በየትኛውም ሀገር ቢሆን ተንደላቆ ተንቀባሮ መኖር የሚያስችለው ደረጃ ነበረው፡፡ ነገር ግን ልጁ ሰው ነውና፣ ባለ ሕሊና ነውና፣ ጭንቅላት ያለው ዜጋ ነውና፣ አስተዋይ ነውና ሕዝቡ ወገኑ በችጋርና በሰብአዊ መብቶች እጦት እየተሰቃየ እያየ የሚበላውና የሚጠጣው ሊዋጥለት አልችል አለው፡፡ ምቾቱ ሊደላው አልቻለም፡፡ በአፍንጫየ ይውጣ አለ፡፡ አለና ድሎት ያለውን ሕይዎቱን መሥዋዕት አድርጎ በአስደናቂ ብቃትና አፈጻጸም የሕዝብን አቤቱታ በተገቢው ቦታና ሁኔታ ለዓለም ሕዝብ አቀረበ አሰማ፡፡

አዎ ይሄም እውነት ነው ረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅን አበራ ከሀዲ ነው፡፡ ግፈኛ አገዛዝን አላገለግልም ብሎ የግፍ አገዛዙን ክዷልና፡፡ ይህ አሁን እሱ ያደረገው ሥራ የሰላማዊ ትግል መሐንዲስ የሆነው ጋንዲ ለስኬት የበቃበት የሰላማዊ ትግል አንዱ ዓይነት እርምጃ ነው፡፡ ከተጠቀምንበትና ሁላችንም ከተባበርን የረዳት አብራሪ ኃይለ መድኅንን አርአያነት ከወሰድን፡፡ ወያኔን በጣት በሚቆጠሩ ቀናት ውስጥ ብቻ እጅ እንዲሰጥ ማድረግ አቅሙን ጨካኝ ጉልበቱን ማሽመድመድ ይቻላል፡፡ እስከመቸ ነው እሽሩሩው? እስከመቸ ነው ትዕግሥቱ? እስከመቸ ነው መቻሉ? መጨረሻ የለውም እንዴ? ልክ የለውም እንዴ? በዚህ ሁኔታ ትውልድ እያለፈ ትውልድ መተካት አለበት እንዴ? ሁሉም ነገር ቢሆን እኮ ልክና መጨረሻ ገደብም አለው፡፡ ትዕግሥታችን እሽሩሩአችን መቻላችን መጨረሻ ገደብና ልክ ካለው ጊዜው አሁን ነው ጊዜው ዛሬ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የምንጨምራቸው ጊዜያት የሚባክኑ ብቻ ሳይሆኑ ህልውናችንን የሚያስከፍሉ የሚበሉ የሚያጠፉ የጥፋት የመዓት ቀናት ጊዜያት ዘመናት ናቸው፡፡

በተናጠል የሚወሰዱ እርምጃዎች የትም አያደርሱንም፡፡ የዚህን ጀግና እርምጃ ዐይተን አድንቀን መቀመጡ ምንም አይጠቅመንም እሱ ትልቁን እርምጃ ተራምዶ ጀምሮልናል የግድ መከተል ይኖርብና፡፡ ይሄኔ ሀገርን ሕዝብን እራሳችንን ነጻ እናወጣለን፡፡ ነጻ ነጻ ነጻ እንሆናለን እኛም ወግ ይደርሰንና ለሥልጣኔ ሽምጥ እንጋልባለን፡፡ የነጻነት ፍሬዎችን ልማትን፣ ሰላምን፣ አስተማማኝ ደኅንነትን፣ ምቾትን፣ ጤናን፣ ፍቅርን እናጣጥማለን እንኮመኩማለን፡፡ ሥጋትን፣ ፍርሐትን፣ ጭቆናን፣ እንግልትን፣ አፈናን፣ እረገጣን፣ መብት መነፈግን፣ ረሀብን፣ ችጋርን፣ ጉስቁልናን፣ አንገት አስደፊውን አዋራጁን ድህነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ቶሎ እናሰናብታለን እንቀብራለን፡፡ ይህች ሀገር ከራሷ አልፋ ለስንት የሚበቃ ሲሳይ በረከት አላት፡፡ ሕዝብ የተቸገረው የተራበው የሚጠማው ስለሌለን አይደለም፡፡ በጨካኝና አንባገነን አገዛዙ ተዘግቶብን፣ ተይዞብን፣ ተቆልፎብን፣ ተከልክለን፣ ተነፍገን ነው እንጂ፡፡ እውነት እንዳይመስላቹህ ድሆች አይደለንም በፍጹም ምንም የሚቸግረን ነገር አልነበረም፡፡

ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!\
http://www.goolgule.com/hailemedhin-and … re.me_aL1F

አንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ!!!

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
================================
በባህር ዳር ከተማ የታየው ህዝባዊ ተቃውሞበሌሎች የሀገራችን ክፍሎችም ተጠናክሮ ይቀጥላል! ===========================
ከአንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ!!!
=========================================
ከጊዜ ወደ ጊዜ አምባገነናዊ የአፈና መዋቅሩን በማጠናከር ለመድብለ ፓርቲ የፖለቲካ ሥርዓት በር መዝጋቱን አጠናክሮ ለብቻው አውራ ፓርቲ ለመሆን እየታተረ ያለው የኢህአዴግ መንግሥት ደርግ በውድቀቱ ዋዜማ ወደ ተላበሰው ባህሪ እየተሸጋገረ እንደሆነ ተስተውሏል፡፡

የዚሁን ድርጅታዊ ባህሪ ውርስ በዋነኛነት ከሚያስፈጽሙት የግምባሩ አባል ድርጅቶች አንዱ የሆነው ብአዴን ኢህአዴግ በአማራው ህዝብ ላይ እየፈፀመው ያለው የንቀት እና የማጥላላት ዘመቻም አብይ ተደርገው ሊወሰዱ ከሚችሉ የግንባሩ አፍራሽ ተግባራት በዋነኝነት ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡

የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የብአዴን ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ አለምነው መኮንን የክልሉን ህዝብ የናቀ እና ያዋረደ አስነዋሪ ንግግር ካደረጉ በኋላ ከጥፋታቸው ከመታረም ይልቅ በክልሉ ቴሌቭዥን ያንኑ አምባገነናዊ ባህሪያቸውን እንደያዙ የግሌ ብቻ ሳይሆን የድርጅቴ አቋም ነው ሲሉ መመለሳቸውም መላውን የሀገሪቷን ህዝብ ያስቆጣ ተግባር ነው፡፡

ይህንን አስነዋሪ ተግባር የፈጸመውን ብአዴንን ከ70 እስከ 80 ሺህ የሚደርሱ የባህር ዳር ከተማና የአካባቢው ነዋሪዎች ከፓርቲያችን ጎን በመሰለፍ እሁድ የካቲት 16 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም የባህር ዳርን ጎዳና እና አደባባዮች በህዝባዊ ማዕበል ሲያስጨንቁ መዋላቸውም ሰላማዊ ትግሉ የደረሰበትን ሁኔታ በግልፅ የሚያስገነዝብ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የኢህአዴግ መንግሥት በአንፃሩ ዛሬም ከስህተቱ ለመማር ያልተዘጋጀ በመሆኑ ይህን የሰፊ ህዝብ ቁጣ በማጣጣል አፋኝ እና ተሳደቢ መሪዎቹን ከጉያው ላለመነጠል እየሞከረ እንደሆነም አስተውለናል፡፡ ፓርቲያችን አንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ አንድነት የባህር ዳር እና አካባቢው ነዋሪዎች ላደረጉት ህዝባዊ ትገል ከፍተኛ ክብር እና አድናቆት አለው፡፡ ይህንን ህዝባዊ መሠረታችንን ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር በሁሉም የሀገራችን ክልሎች ተቃውሞው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ልናረጋግጥ እንወዳለን፡፡

የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ይህንን የህዝብ ጥያቄ አለመቀበሉን እየገፋበት በመሆኑም በባህርዳር የታየው ህዝባዊ ተቃውሞ ቤሎች የሀገራችን ክልሎች ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን አቶ አለምነው መኮንን በፍርድ አደባባይ ለማቆም በአጭር ጊዜ ውስጥ ክስ መስርተን ለህዝብ ይፋ እንደምናደርግ እናረጋግጣለን፡፡

በመጨረሻም በዚህ ፈታኝ የትግል ምዕራፍ ፡-
1ኛ. መላው የኢትዮጵያ ህዝብ
2ኛ. በውጭ ሀገር የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን፤ የፓርቲያችን አባላት እና ደጋፊዎች ከጎናችን በመሆን ትግላችንን እንድትደግፉ ጥሪ እናቀርባለን !!!!
———————————-
በባህርዳር የታየው ህዛባዊ መነቃቃትና የትግል ስሜት በሌሎች የሀገራችን ክፍሎች ይደገማል !!!
—————————–
ድል የህዝብ ነው !!!
የካቲት 20 ቀን 2006 ዓ.ም

ትግሉን ይቀላቀሉ ኪሚሊዮኖች አንዱ ይሁኑ ! እንዴት ካሉ የሚከተለዉን ያንብቡ
======================================

የባህር ዳር ሰልፍ በአስደናቂ ሁኔታ በሰላም ተጠናቋል። ሕዝቡ ከፍተኛ አፈናን ተቋቁሞ፣ ፍርሃትን አዉልቆ የነጻነትን ደዉል አውጇል። ሕዝብ በባህር ዳር ተናግሯል። በዚህ በባህር ዳር ሰልፍ፣ መኢአድ እና አንድነት ሰላማዊ ሰልፍ ስለጠሩ ብቻ አይደለም ሕዝብ የተሰባሰበው። ዉስጥ ዉስጡን ከፍተኛ ድርጅታዊ ሥራ ስለተሰራ፣ ሕዝቡን በወረዳና በቀበሌ ደረጃ ማንቀሳቀስ ስለተቻለ ነው። ድርጅቶች (መኢአድ፣ አድንነት እና ትብብር) በተናጥል ሳይሆን በትብብርና አብሮ በመስራት ስለመሩት ነዉ።

ይህ የባህር ዳር ሰልፍ በየቤታችን ትልቅ ደስታን እንደፈጠረ ይገባናል። ዜጎች በድፍረትና በነጻነት ድምጻቸዉን ሲያሰሙ የመሰለ ደስታ የለም። ሁላችንም ተደስተናል፣ በባህር ዳር ሕዝብም ኮርተናል።

የባህር ዳሩ ሰልፍ ግን ጅማሬ እንጂ ፍጻሜ መሆን የለበትም። ተመሳሳይ እንቅስቃሴዎች እየተደጋገሙ፣ በጥራትና በብቃት፣ በመቀሌ፣ በአዋሳ፣ በድሬደዋ፣ በጂማ፣ በጎንደር፣ በአዲስ አበባ በመሳሰሉ ሌሎች ከተሞች መደረግ አለባቸው። የነጻነት፣ የሰላም፣ የኢትዮጵያዊነት እሳት መቀጣጠል አለበት።

አንድነት/መኢአድ በፊታቸው ከፍተኛ ሥራ አለባቸው። ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል። በባህር ዳር የታየዉን አይነት ሥራ ለመስራት ትልቅ ወጭ አለው። ኢትዮጵያዊ ሁሉ ቀበቶዉን እንዲታጠቅ፣ ትግሉን እንዲቀላቀል፣ የድርሻዉን እንዲወጣ ያስፈልጋል። ከአሁን በኋላ ወደ ኃላ መመለስ የለም። ሰላማዊ በሆነ መንገድ፣ በባህር ዳር እንደተደረገዉ፣ በአገራችን ግዛቶች ሁሉ ሕዝቡን ማደራጀትና ማንቀሳቀስ ያስፈልጋል፤ የግድ ነው። ይቻላልምም።

በባህር ዳር ሁኔታዎች ስለተመቻቹ አልነበረም። የፖለቲካ ምህዳሩ ስለተከፈተ አልነበረም። የመኢአድ እና አንድነት አባላት፣ ደጋፊዎች፣ ታስረዋል፣ ተዋክበዋል ከሥራ ተባረዋል፣ የግድያ ዛቻ ደርሶባቸዋል። ትልቅ ዋጋ ከፍለዋል፤ እየከፈሉም ነዉ። ነገር ግን የተዘጋዉን በር በትግላቸው አስከፍተው ነዉ በባህር ዳር እንዳየነው ሕዝቡን ያንቀሳቀሱት።

በአገር ቤት ያለን ምሁራን፣ ተማሪዎች፣ ሴቶች ፣ ወንዶች ፣ ወጣቶች አረጋዉያን፣ ክርስቲያኑ ፣ ሙስሊሙ፣ ትግሬው፣ አማራዉ፣ ኦሮሞዉ፣ ቅልቅሉ … ሁሉን ኢትዮጵያዊ ከአንድነት ጎን እንዲሰለፍ እንጠይቃለን። አንድነት ጠመንጃ እንደ ሌሎች ጠመንጃ የለውም። አንድነት የፈረንጆችን ጥቅም እንደሚያስጠብቁት እንደ ሌሎች የዉጭ መንግስታት ድጋፍ የለዉም። የአንድነት ኃይልና መተማመኛ ሕዝብ ብቻ ነው።

እንግዲህ

1. አገር ቤት ያለን በአካባቢያችን ወዳሉ የአንድነት ጽ/ቤቶች፣ በዉጭ ደግሞ ያለን የአንድነት ድጋፍ ድርጅቶች በመሄድ እንዴት መርዳትና መተባበር እንዳለብን እንጠይቅ።

2. http://www.andinet.org/ በመሄድ በክሬዲት ካርድ ወይንም ፔይ ፓል የገንዘብ ድጋፍ እናድርግ።

3. የሚሊየነም ድምጽ ለነጻነት ፌስ ቡክ እና የፍኖተ ነጻነት ገጽ ላይክ በማድረግ እየተሰሩ ያሉትን እንከታተል። መልእክቶችን በማስተላለፍ የቅስቀሳቅዎች አካል እንሁን::

https://www.facebook.com/FinoteNestanet https://www.facebook.com/MillionsOfVoicesForFreedomUdj

4. አገር ዉስጥ ላለን በአካባቢያችን የአንድነት መዋቅር ከሌለ፣ በዉጭ ደግሞ የድጋፍ ድርጅት ከሌሉ፣ ሁለት ሶስት ፣ ሆነን እራሳችንን አደራጅተን፣ ፓርቲዉን ፓርቲዉን በማሳወቅ ትግሉን እንቀላቀል። የድጋፍ ድርጅቶች ከሌሉ፣ የአገር ቤቱን ትግሉ የሚደገፉ ሌሎች የሲቪክ ድርጅቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ፣ በነርሱ በኩል ድጋፍ ማድረግ ይቻላል።

5. በግለሰብ ደረጃም በጽሁፍ፣ በሃሳብ መርዳት ከፈለግን [email protected] በሚለው ኢሜል አድራሻ ያሳውቁን።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ አንድ ወቅት እንዳለችዉ፣ ፀሐይ ለኢትዮጵያ ወጥቶላታል። ከአሁን በኋላ አይጨልምም::

Image

Image

አደዋ ደረሰ ጎጠኞች ከፋቸው
ኢትዮጵያዊነት ሊተረክባቸው ።

የአድዋ ድል ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የማንነታችን መሰረትና የህልውናችንም መገለጫ ነው፡፡ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ብቻም ሳይሆን ለመላው የጥቁር ህዝብ የነፃነት ተምሳሌትና የአርነት መስታዎትም ጭምር ነው፡፡ የሰው ልጅ በቆዳው ቀለም ምክንያት መዋረድም ሆነ ማነስ እንደሌለበት፣ ጥቁር ህዝብ በአፈጣጠሩም ሆነ በአስተሳሰቡ ‘ልዩና ድንቅ ነን’ ብለው ከሚኮፈሱት ነጮች ያላነሰ ማንነት እንዳለው፣ ካልነኩት ተንኮል የማይሸርብ ሲነካ ግን በማንነቱ ላይ የማይደራደር ድንቅ ፍጥረት መሆኑ የታየበት ድል ነው የአድዋ ድል፡፡

ዛሬ አለም አብዝታ ስለሰው ልጆች እኩልነት እየሰበከችና በዚህም ስም አያሌ መድረኮችን እያዘጋጀች ቢሆንም ገና ብዙ ያልተፈቱ ተያያዥ ችግሮች እያየን መሆኑ የሚካድ ሃቅ አይደለም፡፡ የአድዋ ድል ግን ገና ያኔ ስልጣኔ ባላደገበት፣ የሰው ልጅ አስተሳሰቡ ባልጎለመሰበት፣ እንኳን ነጮች ጥቁሮች ራሳቸው ባርነት የመፈጠራቸው ዕጣ ፈንታ፣ የአርባ ቀን እድላቸው እንደሆነ አስበው ባርነታቸውን ከእንባቸው ጋር እያጣጣሙ በነበሩበት በዚያ ዘመን… የጥቁርነት ትርጉሙን ፣ የሃገርና ህዝብን ሉአላዊ ክብርን ለመላው አለም በወሬ ሳይሆን በተግባር ያሳየ ዘመን አይሽሬ የመመኪያችን መድረክ ነው የአድዋ ድል፡፡

Image

እነ እስከማውቀው ድረስ የትዊተር አካውንታቸው አልተጠለፈም። ምንሊክ ሳልሳዊ
ሰሞኑን በብአደን ውስጥ የተነሳውን የአቶ አለምነህ እና ተያያዥ የለውጥ ጉዳይ እና የአይሮፕላን ጠለፋ/ እገታ በኢሕአደግ አባላት የተነሱትን እና ሕዝቡ የሚያሰማውን ጉምጉምታ አቅጣጫ ለመቀየር የተደረገ ወያነያዊ የማዘናጊያ ስልት ነው።

ኢትዮጵያውያን ባህላችንን እና የወንጀለኛ መቅጫ ህጋችንን ከድሮም ስለምናውቀው ወይዘሮዋ የተነፈሱ አሊያም የጻፉት ራሳቸው መሆናቸውን በቂ ማረጋገጫዎች ከመኖራቸውም በላይ እነው ራሰ በትዊተር ገጻቸው ላይ መልስ ከመስጠት አንስቶ በግል በመልእክት ሳናግረቸው ያመኑበት መሆኑን አረጋግጠው ሳለ የወያነ መንግስት የሳቸውን ጉዳይ መነጋገሪያ አድርጎ የሰሞኑን ህዝባዊ ጥያቀዎችን በመሸፋፈን ለማዘናጊያነት የተጠቀሙበት ስልት ነው። የትዊተር ገጻቸውን ራሳቸው ዘጉት እንጂ አልተጠለፈም ሃሰት ነው።

ፌስቡክ እና ትዊተር በፍጹም ሊጠለፉ የማይችሉ ሶሻል ኔትወርኮች ናቸው ፣ ያልተማረውን ሰው ያታሉት …https (Hypertext Transfer Protocol Secure ደዲኬቲቭ ሰርቨር የሚባለው ሰርቨር ያላቸው ሲሆን በማይክሮ ሰከን ሁሉንም መረጃዎች ገልብጦ ለማውጣት ፈጣን የሆነ ቅልጥፍና ያለው እና ጠላፊዎች ሲመጡ ለሰኩሪቲ ሲስተም ፕሮቶኮል ኢንጂኒየር የሚጠቁም ኢለመንት ወይንም ኮድ አላቸው ስለዚህ ምንም ነገር ሊደረግ የማይችል ነገር ነው ፣…….. እንደ እኛ አይነት ዌብ ሳይት ያላቸው ሰዎች ቢሉ ይቻላል :: ምክንያቱም የምንጠቀመው የተከራየ ሰርቨር ሲሆን የፈለገ ደዲኬቲቭ ሰርቨር ብንጠቀም በአንድ ሰርቨር ውስጥ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዌብ ሳይቶች ስለሚሞሉበት ለማመልከት ይቸግረዋል …የነ ትውተር እና ፌስቡክ ግን እራሱን የቻለ ሰርቨር ያላቸው ትልቅ ድርጅት ነው ፣እንደዚያማ ቢሆን ኖሮ እንደ እነ ቢቢሲ እና ሲኤን ኤን ያሉ የመረጃ ድርጅቶች ኤፍቢአይን ጨምሮ ትውተር ባልተጠቀሙ ነበር !

አይሮፕላን ተጠለፈ የአቶ አለምነህ ድምጽ ተጠለፈ የወይዘሮ ዘነቡ አካውንት ተጠለፈ ….. አሁን የቀረው ማነው…? ? ? ምንሊክ ሳልሳዊ