በቱርክ ዋና ከተማ ኢስታንቡል የተሰባሰቡ ግብረሰዶማውያን ሊያደርጉት አቅደው የነበረውን ሰላማዊ ሰልፍ የአገሪቱ መንግስት ህገወጥ ነው ሲል በውሃ መርጫ ካኖን መበተኑ ተሰምቷል። ከሰሞኑ በዓለም ላይ እየተከበረ ያለውን የግብረሰዶማውያን ቀን ለማክበር ወጥተው የነበሩት እነዚህ ሰልፈኞች በታቅሲም አደባባይ አቅራቢያ በመሰባሰብ ላይ እንዳሉ በፖሊሶች እንዲበተኑ መደረጉን በስፍራው የነበረ የሮይተርስ ዘጋቢ ተናግሯል። ፓሊሶች የሰልፉ መሪዎችን ካሰሩ በኋላ ከተማዋ ወደ ቀድሞው […]

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ እስር ላይ ቆይተው ሰኔ 15/2007 ዓ.ም በቄራ ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት እንዲፈቱ ተወስኖላቸው ሰኔ 16/2007 ዓ.ም ከእስር ቤት ሲወጡ እንደገና በፖሊስ ተይዘው የታሰሩት ወንይሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤትሄልየም አካለወርቅ ዛሬ ሰኔ 22/2007 ልደታ ፍርድ ቤት 11ኛ ምድብ ችሎት ቀርበው ቀደም ሲል ‹‹ሁከትና ብጥብጥ አስነስተዋል›› […]

አይ ኤስን ለመቃወም ከተጠራው ሰልፍ በኋላ ፖሊስና አቃቤ ህግ በየ ችሎቱ ኢህአዴግ ላይ ሰልፍ በመጥራት ስድብ እያዘነቡበት ነው፡፡ በሚያዝያ 14ቱ ሰልፍ ላይ በቦታው ያልነበሩት የሰማያዊ፣ የቀድሞው አንድነትና የቀድሞው መኢአድ አባላትና አመራሮች እንዲሁም ሌሎች ወጣቶችን ያስሩና እነዚህ ወጣቶች ያላሉትን ክስ ብለው ያቀርባሉ፡፡ ይህ ክስ ደግሞ ለእነሱ የሰልፍ መፈክር መሆኑ ነው፡፡ የስድብ ውርጅብኝ፡፡ በቃ ችሎት የቁጭት መውጫቸው […]

ዛሬ በጥዋት የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ላይ ሊሰጥ የተቀጠረውን ውሳኔ ተመልክቼ ለመዘገብ ልደታ በሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አምርቼ ነበር፡፡ 3፡30 ሰዓት ገደባ በታችኛው መግቢያ በር ጋር ስደርስ፣ ቁጥራቸው በዛ ያሉ፣ የሚሊተሪ ልብስ የለበሱ የጸጥታ ሃይሎች እና የአዲስ አበባ ፖሊሶች በፍርድ ቤቴ ቅጥር ግቢ በር ላይ ሆነው ሰዎችን በጥብቅ እየተፈሹ ሲያስገቡ አስተዋልኩ፡፡ በአጋጣሚ ከጠበቃ […]

‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ እንዲሰፍን እየታገልኩ መሆኔ በክስ ማቅለያነት እንዲወሰድልኝ›› ወጣት ቴዎድሮስ አስፋው በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም መንግስት በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስረው ‹‹ኢህአዴግ ሌባ ነው፣ ህገ መንግስቱ ወረቀት ነው፣ ታፍነናል፣ ታስረናል፣ መለስ የሞተው ደንግጦ ነው፣ ሀይለማሪያም ደሳለኝ በቁሙ የሞተ ነው፣ ቴዎድሮስ ለህዝብ ነው የሞተው›› በሚል ብጥብጥና ሁከት ፈጥራችኋል፣ የሀሰት […]

ኤርትራውያን ስደተኞች አገራቸው ከአፍሪካ ኅብረት አባልነት እንድትሰረዝ ጥያቄ አቀረቡ

በኢትዮጵያ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ሰኔ 19 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢትዮጵያና በተለያዩ አገሮች ባደረጉት የተቃውሞ ሠልፍ፣ በፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሚመራውን የኤርትራ አስተዳደር በማውገዝና ሕጋዊ የሆነ መንግሥት

የማያስተዳድራት አገር የአፍሪካ ኅብረት አባል መሆን እንደማትችል በመግለጽ፣ ኤርትራ ከኅብረቱ አባልነት እንድትሰረዝ ጥያቄ አቀረቡ፡፡

በአዲስ አበባ በሚገኘው የአፍሪካ ኅብረት ዋና መሥሪያ ቤት በመገኘት ቁጥራቸው ከ1,000 የሚበልጡ ስደተኛ ኤርትራውያን ባሰሙት ተቃውሞ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ግንቦት 28 ቀን 2007 ዓ.ም. ኤርትራን በሚመለከት ያወጣውን የሰብዓዊ መብት ረገጣ ሪፖርትን ደግፈዋል፡፡ ‹‹ኢሳያስ አፈወርቂ ከሥልጣን መውረድ አለበት፤›› የሚለውንና ሌሎችንም መፈክሮች በማሰማት፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኤርትራ መንግሥት በተለይ በኤርትራውያን ወጣቶች ላይ እየፈጸመው የሚገኘውን ስቃይ፣ በደልና ሌሎች በዝርዝር ያቀረባቸውን ሪፖርቶች ኅብረቱ እንዲያፀድቀው ጠይቀዋል፡፡

ሕጋዊነት የሌለው መንግሥት የኅብረቱ አባል ሆኖ መቀጠል እንደሌለበት የጠቆሙት ኤርትራውያኑ፣ ፕሬዚዳንቱ ከሥልጣናቸው እንዲወገዱ ኅብረቱ ትኩረት እንዲሰጠው ጠይቀዋል፡፡ 

ለአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ ደብዳቤ ያስገቡ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ለአውሮፓ ኅብረት ጽሕፈት ቤትም ተመሳሳይ ደብዳቤ አስገብተዋል፡፡

የቀይ ባህር አፋር ነፃ አውጭ በሚባለው ድርጅት በተዘጋጀው የተቃውሞ ሠልፍ ላይ ቁጥራቸው ከ30 ሺሕ በላይ የሆኑ ተሳታፊዎች በአዲስ አበባ፣ በሰመራ፣ በዱብቲ፣ በበራ ኃይሌ ካምፕ መገኘታቸው ሲታወቅ፣ በውጭ አገሮች በኒውዮርክና በጄኔቭም የተቃውሞ ሠልፉ መደረጉንም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአዲስ አበባ የተቃውሞ ሠልፍ በማድረግ ለአፍሪካ ኅብረት ያቀረቡትን ደብዳቤ፣ የዶ/ር ድላሚኒ ዙማ ጸሐፊ ተቀብለው፣ ሊቀመንበሯ አስቸኳይ ምላሽ እንደሚሰጧቸው ነግረዋቸዋል፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ግንቦት 28 ቀን 2007 ዓ.ም. ኤርትራን አስመልክቶ ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ፣ በእርስ በርስ ጦርነት እየወደመች ከምትገኘው ሶሪያ ቀጥላ ወጣት ዜጐቿ ወደ ስደት የሚጐርፉባት አገር መሆኗን ገልጿል፡፡

የኤርትራ ሰብዓዊ መብት አጣሪ ኮሚሽን በቀጥታ ኤርትራ ውስጥ ሆኖ በአገሪቱ ዜጐች ላይ የሚደርሰውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት መከታተልና መመራመር ባይችልም፣ ከ550 በላይ ስደተኛ ኤርትራውያንን በማነጋገርና የተለያዩ ጥናቶችን በማድረግ 484 ገጾች ያሉት ሪፖርት ይፋ ማድረጉ ይታወሳል፡፡ 24ኛ ዓመት የነፃነት ቀኗን በቅርቡ ያከበረችው ኤርትራ ላለፉት 24 ዓመታት ዜጐቿ የስቃይ፣ የሞትና የእስራት ሰለባ መሆናቸውን ሪፖርቱ አካቷል፡፡ የሚፈጸሙባቸው የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችም ሆን ተብሎና ታስቦበት የሚደረጉና የዘር ማጥፋትን የሚያካትቱ መሆናቸውን ሪፖርቱ እንደሚያስረዳ መዘገባችን አይዘነጋም፡፡ 

 

በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የኦዲት ሪፖርት አተገባበር ላይ ትችት ቀረበ

የፓርላማው የመንግሥት ወጪ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ተሾመ እሸቱ፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የሚቀርብበትን የኦዲት ትችት ማስተካከል አልቻለም ሲሉ ከፍተኛ ወቀሳ ሰነዘሩ፡፡ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወቀሳውን ተቃውመዋል፡፡

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ በከር ሻሌ የተቋማቸውን የአሥር ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ሰኔ 18 ቀን 2007 ዓ.ም. አቅርበዋል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ በሪፖርታቸው ገጽ 19 ላይ ከተለያዩ አካላት ለመሥሪያ ቤታቸው የተሰጡ አስተያየቶች ትልቅ ጠቀሜታ እንደነበረው ገልጸዋል፡፡ ‹‹የፌዴራል ዋና ኦዲተር በተቋማችን ላይ የሚያደርገውን ኦዲት ተከትሎ የሚላክልን የኦዲት ግኝት ለሥራ አፈጻጸማችን ትልቅ መሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጎልናል፤›› ብለዋል፡፡

የሪፖርት አቀራረብ ትክክል አይደለም ብለው ያመኑት የመንግሥት ወጪ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰበሳቢ አቶ ተሾመ እሸቱ፣ በአቶ በከር ላይ ትችታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

የኦዲት ግኝትን በተመለከተ መቅረብ የነበረበት ሪፖርት በዝርዝር የተወሰደውን ዕርምጃ የሚገልጽ መሆን ነበረበት ያሉት አቶ ተሾመ፣ ይህንን ሕጋዊ ግዴታ ወደ ጎን ትቶ በደምሳሳው የኦዲት ሪፖርቱን ግብዓት አድርገነዋል ብሎ ማስቀመጥ ተገቢ አይደለም ብለዋቸዋል፡፡ 

የፌዴራሉ ዋና ኦዲተርን የሚከታተለው የፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ተሾመ፣ ‹‹ምናልባት የወሰድነውን ዕርምጃ ብንዘረዝር ከፓርላማው ክርክር ይገጥመናል ወይም ሪፖርቱ እንዳይረዝም ብዬ ነው የሚል ምላሽ ይቀርብ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከፋኝ ተብሎ ሕግ አይጣስም፡፡ የከፋን ቀን ሕግ ጥሰን መሄድ አንችልም፤›› ብለዋል፡፡

ችግሩ ለአምስት ዓመታት መቆየቱን ጠቅሰው፣ በዚህ  የሕግ ጥሰት ላይ ምን ዕርምጃ እንደተወሰደ ጠይቀዋል፡፡ ለቀረቡላቸው ትችት አዘል ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት የጀመሩት አቶ በከር፣ ‹‹ዋና ኦዲተር ያቀረበውን ሪፖርት አልካድኩም፤›› ብለዋል፡፡

ዋና ኦዲተር በትክክል ግኝት እንዳገኘ የተናገሩት አቶ በከር፣ ከዋና ኦዲተሩ ጋር በማጠቃለያ ስብሰባ ተነጋግረው ችግሮቹን ማየት መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹ነገር ግን በፖሊሲ አስተዳደር ቦታ ላይ ተቀምጦ ማየትን ይጠይቃል፡፡ ግብር የተጣለበት ከፋይ ቅሬታ አቅርቦ ሲከራከር የተጣለው ግብር ለረዥም ጊዜ ሳይሰበሰብ ይቀራል፡፡ ይህ በኦዲት ቋንቋ ያልተሰበሰ ሒሳብ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ሌላው አምራች ኩባንያዎችን ለመደገፍ የታክስ ክፍያ ጊዜያቸውን እያሰፋንላቸው እንሄዳለን፡፡ ይኼንን በማድረጋችንም ባለሀብቶችን እየደገፍን የመንግሥትን ግብር እያስከፈልን ነው፤›› ብለዋል፡፡

በቂ መረጃ እያለ ያልተሰበሰቡ ገቢዎች መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም  የዋና ኦዲተርን አስተያየት እንደ ግብዓት እየተጠቀሙበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተለያዩ ኬላዎች የተያዙትን የውጭ ገንዘቦችና የከበሩ ማዕድናት በተመለከተ ተገቢውን የሕግ ሥርዓት አለመከተል ተገቢ ባይሆንም፣ ሕግን ባለማወቅ ሠራተኞች የፈጸሙት ስህተት ነው ብለዋል፡፡

 

ከአጋሮቹ ጋር በመሆን የፓርላማውን ወንበሮች ሙሉ በሙሉ ያሸነፈው ኢሕአዴግ፣ ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት አገሪቱ በምትመራበት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውይይት ላይ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን እንደሚያሳትፍ አስታወቀ፡፡ 

ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በተካሄደው ጠቅላላ ምርጫ ኢሕአዴግና አጋር ፓርቲዎች ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸው መገለጹ ይታወሳል፡፡ በዚህ መሠረት በሕዝብ ተወካዮችም ሆነ በክልል ምክር ቤቶች ውስጥ ተቃዋሚዎች ሐሳባቸውን የሚገልጹበት ዕድል ባለመኖሩ፣ ገዢው ፓርቲ ተቃዋሚዎች በአገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲሳተፉ እንደሚመቻች፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንንና የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን አስታውቀዋል፡፡

በዚህ መሠረት በዚህ ሳምንት በመላ አገሪቱ በሚጀመረው የሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውይይት ላይ ተቃዋሚዎች ተሳታፊ ይሆናሉ ተብሏል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ ከሰኔ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ለተከታታይ ስድስት ቀናት በሚካሄደው ውይይት ተቃዋሚዎች እንዲሳተፉ ባይጋበዙም፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትሩ አቶ ሬድዋን ሁሴን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለዕቅዱ ግብዓት ወይም ሐሳብ የሚሰጡበት ራሱን የቻለ መድረክ ይዘጋጃል፡፡ 

‹‹ተቃዋሚዎች ከሕዝብ ጋር ተቀላቅለው ለውይይት ቢቀርቡ ሐሳባቸው ሊዋጥና በሚገባ ላይስተናገዱ ይችላሉ፤›› በማለት አቶ ሬድዋን ተቃዋሚዎች ለብቻቸው መድረክ እንደሚዘጋጅላቸው ገልጸዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ሁለት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተለያዩ ሐሳቦችን አራምደዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ጉዳዩን አጣጥለውታል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ችግር በእንደዚህ ዓይነት መንገድ አይፈታም፡፡ ሥር የሰደደ ችግር አለ ከተባለ ሥር የሰደደ መፍትሔ ነው መቅረብ ያለበት፡፡ ለብ ለብ ሊሆን አይችልም፤›› በማለት በውይይቱ መሳተፍ ኢሕአዴግን እንደማጀብ አድርገው ገልጸዋል፡፡ 

የኢዴፓ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ወንድወሰን ተሾመ በበኩላቸው፣ መንግሥት በዕቅድ ሰነዱ ላይ ለመወያየት ይፋዊ ጥያቄ ያላቀረበ ቢሆንም ኢዴፓ ከመኢአድና ከኢራፓ ጋር በመሆን ሰላማዊ ትግሉ በሚቀጥልበት መንገድ ላይ መምከር መጀመራቸውንና በቅርቡም መግለጫ እንደሚሰጡበት አስታውቀዋል፡፡ በኢዴፓ በኩል መንግሥት ጥያቄ ካቀረበ በሥራ አስፈጻሚው በኩል ውይይት ተደርጎ እንደሚወሰን አቶ ወንድወሰን ተናግረዋል፡፡ 

በአቶ መኮንን ማንያዘዋል በሚመራው ብሔራዊ ፕላን ኮሚሽንና በከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በሚመሩ ኮሚቴዎች የተዘጋጀው ሁለተኛው የአምስት ዓመት ዕቅድ ሰነድ በዘርፍ፣ በዘርፍ ተከፍሎ ለውይይት ይቀርባል፡፡ 

በአዲስ አበባ ከተማ በተዘጋጁት አምስት መድረኮች አቶ ሬድዋን፣ ከንቲባ ድሪባ ኩማና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ ዓባይ ፀሐዬ ውይይቱን ይመራሉ፡፡ 

በክልሎች የሚካሄዱትን የውይይት መድረኮች በተለይ በትግራይ ክልል የሚካሄደውን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ጉዳዮች ክላስተር አስተባባሪና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል፣ በአማራ ክልል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ በኦሮሚያ ክልል በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የመልካም አስተዳደርና ሲቪል ሰርቪስ ክላስተር አስተባባሪና የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሯ ወ/ሮ አስቴር ማሞና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሙክታር ከድር፣ በደቡብ ክልል የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ በሐረሪ ክልል የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ መመደባቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ 

ሁለተኛው የአምስት ዓመት ዕቅድ ሰነድ ውይይት የሚካሄደው በዘርፍ በዘርፍ ተከፋፍሎ ሲሆን፣ ጥሪ ከተደረገላቸው መካከል ወጣቶችና ሴቶች ለየብቻ፣ የግሉ ዘርፍ ተወካዮች፣ የመንግሥት ሠራተኞችና ምሁራን፣ የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችና የአካባቢ ልማት ኮሚቴ ተወካዮች ይገኙበታል፡፡ 

አቶ ሬድዋን እንደገለጹት፣ ከፋፍሎ ማወያየቱ አስፈላጊ የሆነው ሁሉም በተሰማራበት መስክ በቂ ጊዜ ወስዶ ለመነጋገርና ስትራቴጂውን ለማሳካት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ 

ጥሪ የተደረገላቸው ተወያዮችም በኢሕአዴግ መዋቅር ውስጥ ያሉ ብቻ ሳይሆኑ፣ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል የሚወክሉ እንደሆኑ አቶ ሬድዋን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ 

 

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የፌዴራልና የክልል የጋራ ገቢ ተብሎ ከሚሰበሰበው ገቢ ውስጥ ድርሻው እንዲከፈለው ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ያቀረበው ጥያቄ፣ የክልል መንግሥትነት ዕውቅና የሌለው በመሆኑ ውድቅ ተደረገ፡፡

የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 98 የፌዴራሉ መንግሥትንና የክልሎችን የጋራ ታክስና የግብር ሥልጣንን ይደነግጋል፡፡

በዚህም መሠረት የፌዴራል መንግሥትና ክልሎች በጋራ በሚያቋቁሟቸው የልማት ድርጅቶች ላይ የንግድ ትርፍ ግብር፣ የሥራ ግብር፣ የሽያጭና የኤክሳይስ ታክስ በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበስቡ ይገልጻል፡፡ በተጨማሪም በድርጅቶች የንግድ ትርፍ ላይና በባለአክሲዮኖች የትርፍ ድርሻ ላይ የግብርና የሽያጭ ታክስ በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበስቡ፣ በመጨረሻም በከፍተኛ የማዕድን ሥራዎች፣ በማናቸውም የፔትሮሊየምና የጋዝ ሥራዎች ላይ የገቢ ግብርና የሮያሊቲ ክፍያዎች በጋራ እንደሚጥሉና እንደሚሰበሰቡ ይደነግጋል፡፡ 

ይህንኑ ድንጋጌ መሠረት በማድረግ ከሚሰበሰበው የጋራ ገቢ ክልሎች ድርሻቸውን በመውሰድ ለልማት እያዋሉ የሚገኙ መሆኑን፣ በዚሁ አግባብም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የጋራ ገቢ ክፍፍል ድርሻውን እየወሰደ እስከ 2001 ዓ.ም. ድረስ ለልማት ሲያውል መቆየቱን፣ አስተዳደሩ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት በደብዳቤ አሳውቋል፡፡ ከ2001 ዓ.ም. በኋላ ግን የገቢ ድርሻው መቋረጡን በመጥቀስ እንዲለቀቅለት ጥያቄውን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርቧል፡፡ የአስተዳደሩን ጥያቄ ለበጀት ድጐማና የጋራ ገቢዎች ድልድል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የመራው የፌዴሬሽን ምክር ቤት፣ ቋሚ ኮሚቴው ያቀረበለትን የውሳኔ ሐሳብ ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዳምጧል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የትምህርት ሚኒስትሩና የደቡብ ክልል ምክር ቤት ተወካዩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ቋሚ ኮሚቴው በድሬዳዋ አስተዳደር ጥያቄ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም የሚያስፈልገው መሆኑ ስለታመነበት፣ ለሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ እንዲመራ በማድረግ ምላሽ ማግኘቱን አስታውቀዋል፡፡

የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔው ባደረገው ምርመራ ‹‹የኢፌዴሪ መንግሥት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 46(1) መሠረት በክልል መንግሥትነት ዕውቀና የተሰጣቸው ዘጠኙ ክልሎች መሆናቸውን፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 49(1) የፌዴራል መንግሥቱ አካል ተደርጐ የሚወሰደው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው፤›› በማለት መግለጹን አቶ ሽፈራው ገልጸዋል፡፡

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በፌዴራል መንግሥት በወጣ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ቻርተር አዋጅ ቁጥር 416/1996 መሠረት ለጊዜው የፌዴራል መንግሥት አስተዳደራዊ አካል ቢሆንም፣ በሕገ መንግሥቱ በክልልነትም ሆነ በፌዴራል መንግሥት የአስተዳደር መዋቅር ውስጥ የሌለ በመሆኑ የሕገ መንግሥት ትርጉም የሚያስፈልገው ጥያቄ አይደለም በማለት ጉባዔው እንደወሰነ ተናግረዋል፡፡

በዚሁ መሠረትም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ውሳኔውን እንዲያውቀው መደረጉን አቶ ሽፈራው ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡

‹‹በሌላ በኩል ግን ከኅብረተሰቡ የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት አንፃር የከተማ አስተዳደሩ ያቀረበው ጥያቄ አግባብነት ያለው መሆኑን ቋሚ ኮሚቴው ያምናል፤›› ሲሉ አቶ ሽፈራው ተናግረዋል፡፡ 

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የድሬዳዋ ከተማ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ፈቃዱ በየነ የከተማው አስተዳደር በውሳኔው ደስተኛ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ‹‹የድሬዳዋ ከተማ በሕገ መንግሥቱ የክልል መንግሥትነት ዕውቅና እንደሌላት የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን የፌዴራል መንግሥት ከከተማው የሚሰበሰበው ገቢ ተቋዳሽ መሆን አለበት፡፡ ከተማዋ ወደ ኢንዱስትሪ መንደርነት እየተቀየረች ነው፡፡ መሠረተ ልማት ማሟላት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ተጨማሪ ገቢ የከተማው አስተዳደር ሊያገኝ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

ከከተማው የሚሰበሰውን ገቢ የፌዴራል መንግሥት ብቻ እየወሰደ የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በሲሚንቶ ፋብሪካዎች ወይም አሁን በሚፈጠሩት ኢንዱስትሪዎች የሚለቀቅ ጢስና የአካባቢ ጉዳት ገፈት ቀማሽ ብቻ መሆን የለባቸውም ብለዋል፡፡ አስተዳደሩ በካቢኔ ደረጃ ተነጋግሮ ምላሽ የሚሰጥ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡ 

የኦሮሚያ ክልልና የሶማሌ ክልል በድሬዳዋ ላይ ባነሱት የይገባኛል ጥያቄ የፌዴራሉ መንግሥት ባወጣው አዋጅ፣ ድሬዳዋ በጊዜያዊነት የፌዴራሉ መንግሥት መዋቅር አካል እንድትሆን መደረጉ ይታወሳል፡፡  

 

ግንባታው በመገባደድ ላይ ባለው የአዲስ አበባ-ሜኤሶ የባቡር መስመር ላይ በሐዲዶችና በመጋዘን የተከማቹ ንብረተቶች ላይ ተደጋጋሚ የዘረፍ ሙከራ እየተካሄደበት መሆኑ ተጠቆመ፡፡ ፖሊስ መሠረተ ልማቱንም ሆነ በግንባታ የሚሳተፉ

ሠራተኞች ደኅንነት ለማስጠበቅ የተጠናከረ ጥበቃ ማድረጉንና ዘራፊዎችንም ለሕግ ማቅረቡን ገልጿል፡፡

በተለይ በአዳማ ከተማ አካባቢ በመገንባት ላይ ባለው ጣቢያ ተደጋጋሚ ዘረፋ እንደሚፈጽም ተነግሯል፡፡ የጥበቃ ሠራተኞችና ቻይናዊያን ባለሙያዎችም በዘራፊዎች ተኩስ ተከፍቶባቸው እንደነበር ሪፖርተር ሥፍራው ድረስ በመሄድ ለመገንዘብ ችሏል፡፡

በግንባታ ላይ የተሰማሩ ሠራተኞች ዘራፊዎች በጦር መሣሪያ ጭምር በሌሊት ካምፑን ሰብረው በመግባት በመጋዘን የሚገኙ ብረታ ብረቶችንና የግንባታ ግብዓቶችን ለመስረቅ ሙከራ እንደሚያደርጉም ጠቁመዋል፡፡

ከአዲስ አበባ-ሜኤሶ ባለው አጠቃላይ መስመር ላይ አንድ ሻምበል የተጠናከረ ፌዴራል የፖሊስ ኃይል የሚጠበቅ ቢሆንም፣ በአዳማ መጋዘኖች በሚገኙ ቦታዎች ግን ዘራፊዎች ከሠራተኞች ጋር በመመሳጠርም ዘረፋ ለማድረግ መሞከራቸው ተገልጿል፡፡

ግንባታውን እያካሄደ ከሚገኘው የቻይናው ሲአርሲሲ የተገኘ መረጃ፣ ባለፉት ሦስት ዓመታት ከ100 ጊዜ በላይ የዘረፋ ሙከራዎች መፈጸማቸውን ያሳያል፡፡

የአዳማ 03 ቀበሌ አስተዳደር ኃላፊዎች በበኩላቸው፣ ተጠርጣሪ ዘራፊዎችን አድነው በመያዝ ለሕግ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን እስካሁን ድረስ ምን ያህል የዘረፋ ሙከራ እንደተካሄደ ባይገልጹም፣ ሁለት ተጠርጣሪዎች ተይዘው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ መሆኑን አንድ የአዳማ ከተማ አስተዳደር ኃላፊ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ሪፖርተር ከፖሊስ መረዳት እንደቻለው፣ ዘራፊዎች በምርመራ ወቅት ሲጠየቁ የዘረፉት ንብረት የአገሪቱ ሳይሆን የቻይና እንደሆነም አድርገው ይቆጥሩታል፡፡

የጥበቃ ሥራውን እያስተባበሩ የሚገኙት ምክትል ኢንስፔክተር እንግዳው ባዬ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአብዛኛው ሕዝብ ዘንድ የመሠረተ ልማቱን በተመለከተ የተሻለ ግንዛቤ ያለ ቢሆንም፣ በጥቂቶች ዘንድ ያለው ግንዛቤ በተቃራኒው ስለሆነ ሰፊ የግንዛቤ ትምህርት መሰጠት አለበት፡፡

ኩባንያው በበኩሉ በቡድን የተደራጁና የጦር መሣሪያ የታጠቁ ዘራፊዎች በኢትዮጵያውያንና በቻይናውያን ሠራተኞች ላይ በተደጋጋሚ ማስፈራሪያ ሲፈጽሙ፣ በተለያዩ ካምፖች ግንባታ የሚቆምበት ጊዜ እንደነበር ገልጿል፡፡ 

የአገር አቀፍ የባቡር ትስስር አካል የሆነው የሰበታ-ሚኤሶ የባቡር መስመር  ግንባታው በቻይናው ሲአርሲሲ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ 329 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ይኼ ፕሮጀክት በቅርቡ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ለግንባታው 1.8 ቢሊዮን ዶላር በጀት እንደወጣበት ይነገራል፡፡ 

 

ድርጅታቸውን ለመታደግ አገር ቤት የተመለሱት የሆላንድ ካር ባለቤት ያቀረቡት ሐሳብ ውድቅ ተደረገ

በኪሳራ የተዘጋውን ሆላንድ ካር የመኪና መገጣጠሚያ ኩባንያቸውን ለመታደግ፣ ከሦስት ዓመታት ቆይታ በኋላ ግንቦት 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ኢንጂነር ታደሰ ተሰማ፣ ኩባንያውን እንዴት ሊታደጉት እንደሚችሉ

ያቀረቡትን ሐሳብ 201 የሚሆኑ ገንዘብ ጠያቂዎች ውድቅ አደረጉት፡፡

ኩባንያውን ከጨረታ ሽያጭ ያድናል ያሉትን ዕቅድ ነድፈውና ለመንግሥት አቅርበው ተቀባይነት በማግኘታቸው ወደ አገር ቤት የተመለሱት ኢንጂነር ታደሰ፣ ስድስት ሚሊዮን ብር ይዘው መምጣታቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

201 የሚሆኑት የኩባንያው ደንበኞች መኪና ለመግዛት ከ62 ሚሊዮን ብር በላይ ክፍያ የፈጸሙ ቢሆንም፣ ኩባንያው በገባው ቃል መሠረት ሊፈጽም ባለመቻሉ ኪሳራ አሳውጆ ነበር፡፡

ቁጥራቸው 201 መሆናቸው የተጠቀሰው ገንዘብ ጠያቂዎች፣ ሰኔ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. የኩባንያው ባለቤት፣ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሬጅስትራርና የተለያዩ ኮሚቴዎች ተሰብስበው በኩባንያው ባለቤት ሐሳብ ላይ ውሳኔ አስተላልፈዋል፡፡

በጠበቃቸው አቶ ጥላሁን ምትኩ አማካይነት የኩባንያው ባለቤት ሐሳብ ተገልጿል፡፡ በዚህም መሠረት ኩባንያው ከኪሳራ ወጥቶ የባለገንዘቦቹን መብት እንደሚያስጠብቅ፣ በመገጣጠሚያ ፋብሪካው ውስጥ ያሉ 174 መኪኖችን ገጣጥሞ ለገበያ ለማቅረብ ስድስት ሚሊዮን ብር እንደተዘጋጀ፣ ተሽከርካሪዎቹ ተገጣጥመው እስከሚሸጡ ድረስ ንብረቶቹ በሙሉ በንብረት ጠባቂና መርማሪ ዳኛ ሥር እንደሚቆዩ ተናግረው፣ በሐራጅ ቢሸጡ ግን የሚገኘው ገንዘብ ከመንግሥት ግብር፣ ከባንክ ዕዳ፣ ከሠራተኞች ክፍያና ከንብረት ዕዳ ማጣሪያ ክፍያ እንደማይተርፍ በመግለጽ፣ በኢንጂነሩ ሐሳብ መስማማት ምርጫ የሌለው መሆኑን ጠበቃው አብራርተዋል፡፡ 

ገንዘብ ጠያቂዎቹ በበኩላቸው በሰጡት ምላሽ እንዳብራሩት፣ ኢንጂነር ታደሰ ያቀረቡት ሐሳብ ቀደም ብሎ በእንግሊዝኛ ካቀረቡላቸው የሚለየው በአማርኛ መቅረቡ ነው፡፡ የቀረበው የአፈጻጸም ዕቅድ ተዓማኒ እንዳልሆነና ለገንዘብ ጠያቂዎቹ ገንዘባቸው እንዴት እንደሚመለስና ምን ያህል ወለድ እንደሚያካትት አይገልጽም፡፡ ለ174 መኪናዎች መገጣጠሚያ ብለው ያቀረቡት ገንዘብ፣ ባለአንድ ፎቅ የሆነ ቤት እንኳን መግዛት አይችልም ብለዋል፡፡ ኩባንያው ሐሳብ ሲያቀርብ ስለዕዳው አከፋፈል በቅድሚያ የገንዘብ ዋስትና ማቅረብ ቢኖርበትም አለማቅረቡን፣ የከሰረው ኩባንያ ከፍተኛ ዕዳ ቢኖርበትም ከባንክና ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከፍተኛ ግብር ከፋዮች መሥሪያ ቤቶች ጋር ምን ዓይነት ስምምነት ላይ እንደደረሰ ባለማሳወቁ፣ ሐሳቡን ለመቀበል እንደማይችሉ አስረድተዋል፡፡

የከሰረው ኩባንያ ንብረት ጥበቃ ሹም አቶ ግርማ ዓለሙ የሚባሉት ግለሰብ ደግሞ፣ የኢንጂነር ታደሰን ሐሳብ ሌላ ጊዜ ጽፈው ከሚያቀርቡት የተለየ አለመሆኑን ተናግረው፣ የመክሰር ሥርዓት ሒደቱን ለማቋረጥና በስምምነት ሐሳቡ ለመቀጠል የሚያስችል፣ በንግድ ሕጉ ያሉ አስገዳጅ ሁኔታዎችን አሟልተው አለመቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ስድስት ሚሊዮን ብር እንዳቀረቡ ኢንጂነሩ ቢናገሩም፣ በቅድሚያ መፍትሔ ማግኘት ያለባቸው የቀድሞ ሠራተኞች ክፍያ፣ የፎርክሎዠር (በሐራጅ የመሸጥ) መብት ያለው ዘመን ባንክ ብድር ጉዳይና ለሌሎች የመንግሥት ክፍያዎች የሚበቃ ገንዘብ ስለመኖሩ ተጨባጭ ማረጋገጫ እንደሌለ ገልጸዋል፡፡

በንግድ ሕግ ቁጥር 1064(3) መሠረት የስምምነት ሐሳቡ በኩባንያው ሥልጣኑ በተሰጠው አስተዳዳሪ የፈረመበት ሆኖ ባለመገኘቱ፣ የኢንጂነር ታደሰ ውክልና ሥልጣን የተሰጣቸው ስለመሆኑ ማስረጃ ማቅረብ ስላልቻሉ፣ ሐሳቡ ተቀባይነት እንደሌለውም ተናግረዋል፡፡

በሕግ መሟላት የሚገባቸው ነገሮች ሳይሟሉ ስምምነት ላይ ቢደረስና ሥራ ቢጀመር፣ ንብረቶች ሊሸሹና ሊጠፉ ስለሚችሉ ሊመለስ የማይችል ጉዳት ሊደርስ እንደሚችልም አክለዋል፡፡

በመጨረሻም በውይይቱ ላይ የተለያዩ አስተያየቶች በመቅረባቸው ድምፅ እንዲሰጥበት ተደርጐ፣ በዕለቱ የተመዘገቡ 201 ግለሰቦች ወይም 62,516,068 ብር ካላቸው ገንዘብ ጠያቂዎች ውስጥ 54,982,120 ብር ያላቸው 134 ሰዎች ሐሳቡን ውድቅ አድርገውታል፡፡ በመሆኑም በንግድ ሕግ ቁጥር 1084 (1) መሠረት የስምምነት ሐሳቡ ተቀባይነት አለማግኘቱን፣ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዋና ሬጅስትራር አቶ መሠረት አያሌው በፊርማቸው አረጋግጠዋል፡፡    

 

የዛይ ሕዝብ የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ አቅርቧል

የአማራ ክልል ምክር ቤት የቅማንት ሕዝብ ላነሳቸው ተጨማሪ የማንነትና ራስን የማስተዳደር ጥያቄ፣ ከዚህ ቀደም ዋናውን ችግር ለመፍታት በሄደበት መንገድ እንዲፈታ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ አሳለፈ፡፡ 

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የመጨረሻ የሥልጣን ዘመኑን ማጠቃለያ ጉባዔ ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ባካሄደበት ወቅት፣ የምክር ቤቱ የሕገ መንግሥትና ክልሎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ በቅማንት ሕዝቦች የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ላይ ያቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ ነው ውሳኔውን ያሳለፈው፡፡ 

በአማራ ክልል የሚኖሩ የቅማንት ሕዝቦች የማንነትና ራስን የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄያቸውን በመጀመርያ ያቀረቡት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው፡፡ ምክር ቤቱም ለቀረበው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ኃላፊነቱን እንዲወስድ ማድረጉን የቋሚ ኮሚቴው ሪፖርት ያስታውሳል፡፡ 

ቋሚ ኮሚቴው የጥናት ቡድን አቋቁሞ ከአማራ ክልል፣ ከሰሜን ጎንደርና በየደረጃው ከሚገኙ የወረዳና የቀበሌ አመራሮችና ከአቤቱታ አቅራቢ ኮሚቴ ጋር በመተባበር ጥናት ማካሄዱን ይገልጻል፡፡ በዚሁ ጥናት በላይ አርማጭሆ፣ በጭልጋና በመተማ ወረዳዎች የወረዳ አመራሮችና የጥያቄ አቅራቢው ሕዝብ አስተባባሪ ኮሚቴ በመስማማት በመረጧቸው ናሙና ቀበሌዎች ባደረገው ጥናት ዕድሜ ጠገብ አዛውንቶች፣ አልፎ አልፎም ወጣቶች ቋንቋውን እንደሚናገሩና ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ሕፃናት ቋንቋውን ለመማር ከፍተኛ ጉጉት እንዳላቸው የጥናት ቡድኑ ማረጋገጡን የኮሚቴው ሪፖርት ይገልጻል፡፡ 

በጥናቱ ያልተሸፈነ ነው ያለውን ማኅበረሰቡ በተያያዘ መልከዓ ምድር መኖር ያለመኖራቸውን ያካተተ ጥናት ተጠንቶ እንዲቀርብለት ቋሚ ኮሚቴው ለጥናት ቡድኑ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውሷል፡፡ 

የጥናት ቡድኑ ከላይ በተገለጸው መሠረት ጥናቱን ለመቀጠል በተንቀሳቀሰበት ወቅት፣ የክልሉ መንግሥት በራሱ ተነሳሽነት ለጥያቄው ምላሽ ለመስጠት ኮሚቴ አቋቁሞ ሥራ መጀመሩን ገልጿል፡፡ በቋሚ ኮሚቴው የተላኩ አጥኚዎች ተልዕኮ ለጊዜው እንዲቆይና የክልሉ መንግሥት በራሱ ጥያቄውን ለመመለስ የጀመረው እንቅስቃሴ ውጤት እንዲጠበቅ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት፣ ጥያቄውን ቋሚ ኮሚቴው እንደተቀበለው ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡ 

ክልሉ ባካሄደው ጥናት የራስ አስተዳደር ጥያቄውን ዕውቅና ሰጥቶ የቅማንት ሕዝብ ራሱን ችሎ በኩታ ገጠም በሚኖርባቸው የጭልጋና የላይ አርማጭሆ ወረዳዎችን ማዕከል በማድረግ፣ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ጀምሮ የአስተዳደር በጀት ለመመደብና ሌሎች አስፈላጊ ሥራዎችን ለመሥራት የአማራ ክልል ምክር ቤት በ14ኛ መደበኛ ጉባዔው ውሳኔ ማሳለፉን በመግለጽ፣ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሪፖርት ማድረጉን ቋሚ ኮሚቴው ገልጿል፡፡ የክልሉ መንግሥት ችግሩን ለመፍታት በተነሳሽነት ያሳየው ትብብርና ቁርጠኝነትን የፌዴሬሽን ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ አድንቆታል፡፡ 

ይሁን እንጂ የማኅበረሰቡ ተወካዮች የክልሉ ምክር ቤት የሰጠው ውሳኔ ሁሉንም ቀበሌዎች ያላካተተና የተሸራረፈ ውሳኔ ነው በማለት ተቃውሟቸውን በድጋሚ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ማቅረባቸውን፣ የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሪፖርት ይገልጻል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው በጥያቄው ላይ ውይይት በማድረግ የቀረበውን ተጨማሪ ጥያቄ ክልሉ ከዚህ በፊት ከፈታው ችግር በላይ ሊሆን እንደማይችል ግንዛቤ በመውሰድ፣ የክልሉ መንግሥት በጀመረው አግባብ ተጨማሪ ጥያቄውን እንዲፈታ የሚል አቋም በመያዙ የፌዴሬሽን ምክር ቤትም ይህንን ውሳኔ በመቀበል ለክልሉ ኃላፊነቱን በመስጠት እንዲወስን ሲል ጠይቋል፡፡ በቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ላይ በመወያየትም ምክር ቤቱ ውሳኔውን ተቀብሎ አፅድቆታል፡፡ 

የቅማንት ሕዝብ በአማራ ክልል በስምንት ወረዳዎች በሚገኙ 126 ቀበሌዎች ውስጥ የራስ አስተዳደር ጥያቄ ያነሰ ቢሆንም፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ግን ባካሄደው ጥናት ላይ ተመሥርቶ መጋቢት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. የሰጠው ውሳኔ በሁለት ወረዳዎች በሚገኙ 42 ቀበሌዎች ላይ ነው፡፡ የቅማንት ሕዝብ ተወካዮች ለሪፖርተር በጽሑፍ እንደገለጹት፣ የክልሉ መንግሥት ጥያቄያቸውን እየሸራረፈና ተጨማሪ ጥያቄዎችን እያነሱ ባሉት ተወካዮች ላይ ጉዳት እያደረሰ ነው፡፡ 

‹‹ከዚህ ሁሉ የችግር ጫና ውስጥ የቅማንት ሕዝብ እየገባ ያለው ጥያቄው በይግባኙ መሠረት በፌዴሬሽን ምክር ቤት መመለስ ባለመቻሉ ነው፡፡ ይግባኝ የቀረበለት የፌዴሬሽን ምክር ቤት በአዋጅ ቁጥር 251/1993 በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት የማያዳግም ውሳኔ ቢያስተላልፍ ይህ ሁሉ ችግር ውስጥ አይገባም ነበር፡፡ አሁንም በቀረበለት ይግባኝ መሠረት ውሳኔ እንዲያስተላለፍ አቤቱታችንን እናሰማለን፤›› ሲሉ ሰኔ 9 ቀን 2007 በጻፉት ደብዳቤ ፌዴሬሽን ምክር ቤትን ጠይቀዋል፡፡ 

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ መንግሥትና የክልል ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ግን በአዋጁ መሠረት ኃላፊነት ቢኖረውም፣ ለክልል መንግሥታት ቀርበው ውሳኔ በተሰጠባቸው የማንነት ጥያቄዎች ቅር በመሰኘት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የሚቀርቡ አቤቱታዎችን በመመርመር፣ በምክር ቤቱ የውሳኔ ሐሳብ እንደሚያቀርብ በተሻሻለው የምክር ቤቱ የአሠራርና የአባላት ሥነ ምግባር ደንብ ቁጥር 1/1999 ኃላፊነት የተሰጠው በመሆኑ የክልሉን ውሳኔ በመመርመር እንደተቀበለው ገልጿል፡፡ 

ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ኃላፊነት በመውሰድ ጥናት ጀምሮ የነበረው አጥኚ ቡድንና የክልሉ ምክር ቤት ባካሄደው ጥናት ላይ በመመሥረት ያሳለፈው ውሳኔ ተመሳሳይነት ያላቸው በመሆኑ፣ ተጨማሪ ጥያቄውን የክልሉ መንግሥት በቀደመው አግባብ ቢመልሰው ችግር እንደማይኖረውም ቋሚ ኮሚቴው እምነቱ እንደሆነ ገልጿል፡፡ 

ይህ በእንዲህ እንዳለ በኦሮሚያ ክልል ዝዋይ ሐይቅ ደሴት ላይ የሚኖሩት የዛይ ማኅበረሰብ የማንነትና ራስን የማስተዳደር ጥያቄ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርበዋል፡፡ የምክር ቤቱ የሕገ መንግሥትና የክልሎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባዔ፣ የክልሉ መንግሥትና ምክር ቤት የዛይ ማኅበረሰብ ጥያቄን በተመለከተ ውይይት እያደረጉ መሆኑን በመጥቀሳቸው ጉዳዩ ለክልሉ ተትቷል፡፡ 

 

በደቡብ ክልል በጋብቻ ምክንያት በሐዲቾና በወላቢቾ ጎሳዎች መካከል የተቀሰቀሰውን ከፍተኛ ግጭት፣ የክልሉ ፖሊስ በአስቸኳይ እንዲቀርፍና ጥፋተኞችን ለሕግ እንዲያቀርብ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አሳሰበ፡፡ 

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ለደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በጻፈው ደብዳቤ፣ የፌዴራል ፖሊስን ወደ አካባቢው ማሰማራት አግባብነት እንደሌለው፣ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ሰላምና ፀጥታ ለማስፈን በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት ኅብረተሰቡ ተረጋግቶና ደኅንነቱ ተጠብቆ እንዲኖር ለማድረግ የሕዝብ አደራና ኃላፊነቱን እንዲወጣ አሳስቧል፡፡ 

በዚህ የጎሳ ግጭት ተሳታፊ የሆኑት ሕገወጥ ድርጊት ፈጻሚዎች ላይ ምርመራው ተጣርቶ ለሕግ እንዲቀርቡ፣ የተፈናቀሉ ዜጎችም ወደ ቀድሞ መኖሪያ ቤታቸው እንዲመለሱ እንዲደረግ አሳስቧል፡፡ 

በሒዲቾና በወላቢቾ ጎሳዎች መካከል ግጭቱ የተቀሰቀሰው ከግንቦት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ወዲህ ሲሆን፣ ምክንያቱ ደግሞ የሐዲቾ ጎሳ አባል የሆነ ግለሰብ ከወላቢቾ ጎሳ አባል ከሆነች አንዲት ግለሰብ ጋር በመጋባቱ ነው፡፡ 

ይህንን ጋብቻ ያልተቀበሉ የወላቢቾ ጎሳ አባላት፣ ‹‹እንዴት አናሳ ዘር ከእኛ ዘር ይጋባል?›› በማለት በአንድ ላይ በመነሳት በሐዲቾ ጎሳ አባላት ላይ ጥቃትና የንብረት ውድመት መፈጸማቸውን ከአካባቢው ለፌዴራል መንግሥት ተቋማት አቤት ለማለት ተወክለው የመጡ ግለሰቦች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ 

የወላቢቾ ነዋሪዎችን ቤቶችና ንብረቶች በማቃጠልና ያገኙትን በመደብደብ፣ በበርካታ ነዋሪዎች ላይ ጉዳት ከማድረሳቸው በተጨማሪ ሰዎችን መግደላቸውን ተወካዮቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ 

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የወንዶ ገነት ወረዳ ፖሊስ ኃላፊ የተፈጠረው ግጭት በአሁኑ ወቅት መቀረፉን ገልጸው፣ የሞተ ሰው አለ መባሉን አስተባብለዋል፡፡ 

የፖሊስ ኃላፊው ይህንን ይበሉ እንጂ፣ የሐዲቾ ጎሳ አባላት በርካቶቹ እስካሁን ወደ መኖሪያቸው እንዳልተመለሱና አሁንም ሥጋት ውስጥ መሆናቸውን ተወካዮቹ ይናገራሉ፡፡  

 

በመጪዎቹ ሦስት ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ተገንብተው አገልግሎት መስጠት ይጀምራሉ ተብለው የሚጠበቁ ስምንት የዓለም አቀፍ ብራንድ ሆቴሎች መምጣትን ተከትሎ፣ ኢትዮጵያ ከአሥር ዋና ዋና የአፍሪካ አገሮች ውስጥ አንዷ

ለመሆን እንደቻለች ታወቀ፡፡ በአፍሪካ በሆቴል ኢንቨስትመንት ውስጥ ስማቸው ከሚጠቀስ ኩባንያዎች መካከል ሒልተን ዓለም አቀፍ፣ በአዳዲስ ሆቴሎች ግንባታና በመኝታ ክፍሎች ብዛት ቀዳሚውን ሥፍራ መያዙን ጥናቶች ጠቁመዋል፡፡ 

ላለፉት አራት ዓመታት ‘አፍሪካ ሆቴል ኢንቨስትመንት ፎረም’ በሚል ርዕስ ዓመታዊ ጉባዔ በማካሄድ ላይ የሚገኘው የእንግሊዙ ቤንች ኤቨንትስ ይፋ ባደረገው ጋዜጣዊ መግለጫ መሠረት፣ በኢትዮጵያ የሚገነቡት ስምንት ሆቴሎች በጠቅላላው ከ1,300 በላይ ክፍሎች እንደሚኖሯቸው ይጠበቃል፡፡ በአንፃሩ በአፍሪካ ከ270 በላይ ሆቴሎች እንደሚገነቡ ሲጠበቅ፣ ከ30 ሺሕ ያላነሱ ክፍሎች እንደሚይዙም ቤንች ኤቨንትስ ጥናቶችን ጠቅሶ ያሠራጨው መግለጫ ያመለክታል፡፡ 

በአፍሪካ ግብፅ በ18 አዳዲስ ሆቴሎች ግንባታ የመጀመሪያውን ረድፍ በመያዝ እየመራች ትገኛለች፡፡ ሞሮኮ፣ ናይጄሪያ፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዝያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሊቢያ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያና ሩዋንዳ በቅደም ተከተል ከአንድ እስከ አሥር ያለውን ደረጃ በመያዝ ግብፅን ይከተላሉ፡፡ በእነዚህ የሆቴል ግንባታዎች ላይ ትልቁን ድርሻ የያዘው ሒልተን ዓለም አቀፍ መሆኑም ታውቋል፡፡ በክፍሎች ብዛት ቀዳሚነቱን የያዘው ሒልተን ከ7,200 በላይ ክፍሎች ያሏቸውን 29 ሆቴሎች በአፍሪካ እየገነባ እንደሚገኝ ሲገለጽ፣ ማሪዮት ሆቴል በበኩሉ በ36 ሆቴሎች እየመራ ቢሆንም፣ በክፍሎች ብዛት ግን 6,412 ላይ በመወሰኑ ከሒልተን ባሻገር በካርልሰን ሬዚዶር ተቀድሟል፡፡ 

በሌላ በኩል ከወራት በፊት በአዲስ አበባ ተካሂዶ ዓለም አቀፍ ትኩረትን ስቦ የነበረው የአፍሪካ ሆቴል ኢንቨስትመንት ፎረም፣ በመጪው ዓመት መጀመሪያ ላይ በድጋሚ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ መዘገባችን ይታወሳል፡፡

የፎረሙ አዘጋጆች ከወራት በፊት ለሪፖርተር እንዳስታወቁት፣ ለአራተኛ ጊዜ ተካሂዶ በነበረው ፎረም ሪከርድ የሰበረ ተሳትፎና ያልተጠበቀ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱ በአዲስ አበባ በድጋሚ እንዲካሄድ ለመወሰን ምክንያት ሆኗል፡፡ ከዚህም ባሻገር በሆቴልና በሌሎች የኢንቨስትመንት መስኮች የተሰማሩ ትልልቅ ኩባንያዎች ያሳዩት ፍላጎትና ተሳትፎም ጉባዔው በድጋሚ አዲስ አበባ እንዲካሄድ ማስገደዱን፣ ፎረሙን የሚያዘጋጀውና መገኛው እንግሊዝ የሆነው ቤንች ኤቨንትስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ማቲው ዌይስ ገልጸው ነበር፡፡ 

ከአምስት ዓመት በፊት ጀምሮ የአፍሪካ ሆቴሎች ኢንቨስትመንት ፎረም በአዲስ አበባ እንዲካሄድ ለማድረግ ሲንቀሳቀስ የቆየው አገር በቀሉ ካሊብራ ሆስፒታሊቲ ኮንሰልታንሲ ኤንድ ቢዝነስ ኩባንያ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡ ስለፎረሙ በድጋሚ መምጣት ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው የካሊብራ አማካሪ ኩባንያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ነዋይ ብርሃኑ፣ በመጪው ዓመት መስከረም ወር አጋማሽ ላይ እንዲካሄድ ቀነ ቀጠሮ የተያዘለት ፎረም እንዲመጣ መወሰኑ እንደማይቀር ከዚህ ቀደም የታየው ስኬታማ ዝግጅት ጠቋሚ እንደነበር መግለጻቸው አይዘነጋም፡፡

ከሆቴሎች ባሻገር በካሊብራ አማካሪ ኩባንያ በኩል ድርድር እያደረጉ ከሚገኙ መካከል ሦስት ተጨማሪ ሆቴሎች፣ ቀጣዩ ፎረም ከመካሄዱ በፊት ስምምነት ይፈጽማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አቶ ነዋይ ለሪፖርተር መግለጻቸውን በመጥቀስ መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ለሁለተኛ ጊዜ በሸራተን አዲስ ይካሄዳል ተብሎ ለሚጠበቀው ፎረም፣ በቅርቡ ሥራ የጀመረው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅትና የኢትዮጵያ ቱሪዝም ምክር ቤት እንቅስቃሴ መጀመራቸው ተሰምቷል፡፡ ቤንች ኤቨትንስ ኩባንያም ለእነዚህ መንግሥታዊ ተቋማት ፎረሙ በድጋሚ በአዲስ አበባ እንዲካሄድ የኩባንያው ቦርድ መወሰኑን በደብዳቤ እንዳሳወቃቸው ታውቋል፡፡

በዚህ ቀደም የተካሄዱትን የአፍሪካ ሆቴል ኢንቨስትመንት ፎረሞችን ሞሮኮ አንድ ጊዜ፣ ኬንያ ሁለት ጊዜ ያስተናገዱ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ መጪውን ጨምሮ ለሁለተኛ ጊዜ በማስተናገድ ኬንያን ትስተካከላለች፡፡ ከስድስት መቶ በላይ ተሳታፊዎች፣ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ ዓለም አቀፍ ሆቴሎችና አማካሪዎች፣ እንዲሁም የሆቴል አስተዳዳሪዎች በስፖንሰርነት የታሰተፉበት ከፍተኛው ፎረም በአዲስ አበባ መካሄዱን ቤንች ኤቨንትስ አስታውቋል፡፡ በመጪው ፎረም በስፖንሰርነት ለመሳተፍ ከወዲሁ ከተመዘገቡት መካከል ሰንሻይን ኮንስትራክሽን ኩባንያ ግንባር ቀደምት ሆኗል፡፡ 

በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ብራንድ ያላቸው ሆቴሎች ቁጥር ሦስት ብቻ መሆናቸውን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በመጪዎቹ አምስት ዓመታት አገሪቱ ይኖራታል ተብሎ የሚጠበቀው ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን የሚያሟሉ ብራንድ ሆቴሎች ቁጥር በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር ትንበያዎች ይጠቁማሉ፡፡ በአገሪቱ ያሉ ጠቅላላ ባለ ኮከብ ሆቴሎች ቁጥር 120 ሲሆን፣ ያሏቸው የመኝታ ክፍሎች ብዛትም ከአንድ ሺሕ በታች ነው፡፡ 

 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከግንቦት 1988 እስከ ሚያዝያ 1997 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ጊዜያት በሕገወጥ መንገድ የተያዙ ይዞታዎችን ሕጋዊ ለማድረግ ባወጣው መመርያ ለመስተናገድ ከቀረቡ 91 ሺሕ ጥያቄዎች፣ ለተወሰኑት ሕጋዊ ካርታ ተሰጠ፡፡ 

የአዲስ አበባ ይዞታ አስተዳደር ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት የቀረቡለት ጥያቄዎች ላይ ባካሄደው ማጣራት 32 ሺሕ የሚጠጉት ጥያቄዎች ቦታውን የያዙት ከ1997 ዓ.ም. በኋላ በመሆኑ ውድቅ ሲያደርግ፣ በበጀት ዓመቱ ለአምስት ሺሕ ሕገወጥ ባለይዞታዎች ሕጋዊ ካርታ መስጠቱ ታውቋል፡፡  

የአዲስ አበባ ከተማ ይዞታ አስተዳደር ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ደረጀ ላቀው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በሕገወጥ መንገድ የተያዙ ቦታዎች 44,547 ናቸው፡፡ ነገር ግን ምዝገባ በሚካሄድበት ወቅት ከ91 ሺሕ በላይ ጥያቄዎች መቅረባቸውን አቶ ደረጀ ገልጸው፣ 32 ሺሕ ያህሉ በመመርያው መሠረት ሊስተናገዱ የማይችሉ ናቸው ብለዋል፡፡

በዚህ ወር መጨረሻ በሚጠናቀቀው የበጀት ዓመት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ አምስት ሺሕ ቦታዎች ሕጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ሰጥቷል፡፡ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ አጠቃላይ ሥራውን በዚህ በጀት ዓመት የማጠናቀቅ ዕቅድ ቢኖረውም፣ የማጣራት ሥራው በመብዛቱ በሚቀጥለው በጀት ዓመት ቀጣይ ሥራዎች እንደሚኖሩ አቶ ደረጀ አስረድተዋል፡፡

ከ1988 እስከ 1997 ዓ.ም. ባለው ጊዜ የተያዙ ይዞታዎች ቢሆኑም፣ ከማስተር ፕላኑ ጋር የሚቃረኑ በመሆናቸው 2,346 ባለይዞታዎች ምትክ ቦታ እንዲሰጣቸው ለመሬት ባንክና ማስተላለፍ ኤጀንሲ መላካቸውን አቶ ደረጀ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ከሕጋዊ ይዞታ ውጪ አስፋፍተው መሬት ከያዙና የይጠቃለልኝ ጥያቄ ካቀረቡ 14 ሺሕ ባለይዞታዎች ውስጥ፣ 3,160 የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንደታተመላቸው፣ ከሁለት ሺሕ በላይ የሚሆኑት ከማስተር ፕላኑ ተቃርኖ ያለው ይዞታ አጠቃለው በመያዛቸው ጥያቄዎቻቸው ተቀባይነት እንዳላገኙ አስታውቀዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ1988 ዓ.ም. በፊት የተያዙ 65 ሺሕ ሰነድ አልባ ይዞታዎች ጥያቄ ማስተናገዱም ይታወቃል፡፡ ከዚህ በኋላ ከ1988 እስከ 1997 ዓ.ም. ድረስ የተያዙ ቦታዎች ከማስተር ፕላኑ ጋር ተቃርኖ የሌላቸው መሆኑ ከተረጋገጠ እንዲያስተናግዱ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

ነገር ግን አሁንም ቢሆን ከ1997 ዓ.ም. በኋላ በሕገወጥ መንገድ ይዞታ የያዙ ግለሰቦች መንግሥት እንዲያስተናግዳቸው በመጠየቅ ላይ ይገኛሉ፡፡

 

በነ ዘመነ ካሴ መዝገብ የተከሰሱት 5 የመኢአድ አባሎች ናቸው አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርብላቸው ነው የጠየቁት የተከሰሱት የግንቦት 7 አባል ናችሁ ተብለው ነው በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ስልጠና ተሰጥቷችሁ የሽብር ተግባር ለመፈጸም ስትንቀሳቀሱ ነበር ተብለው ላለፉት ሁለት አመታት በእስር የሚገኙት እነዚህ ተከሳሾች አንዳርጋቸው ፅጌ የሚባል ሰው አናውቅም አንዳርጋቸው አሱ አውቃቸዋለሁ አሰልጥኛቸዋለሁ የሚል ከሆነም በናንተ ቁጥጥር ስር […]

መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ እስር ላይ ቆይተው እንዲፈቱ ተወስኖላቸው ከእስር ቤት ሲወጡ እንደገና በፖሊስ ተይዘው የታሰሩት ወንይሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤትሄልየም አካለወርቅ ላይ ፖሊስ አዲስ ክስ አቀረበ፡፡ እነ ወይንሸት ሰኔ 18/2007 ዓ.ም ቀደም ብለው ተከሰውበት በነበረው ተመሳሳይ ‹ወንጀል› ፖሊስ የምርመራ መዝገብ ይዞ ቀደም ብለው ውሳኔ ባገኙበት በተመሳሳይ ቄራ ፍርድ ቤት ቀርበው ዳኞቹ ‹‹እኛ ፈርደናል፤ እንዲለቀቁም […]

የእንግሊዝ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዛሬ ሐሙስ ሰኔ 18/2007 ዓም በአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ባወጣው መግለጫ የኢህአዴግ/ወያኔን መንግስትን ማስጠንቀቁን ሮይተርስ ዘገበ አቶ አንዳርጋቸው የህግ ድጋፍ በማያገኙበትና ይግባኝ ሊጠይቁ በማይችሉበት ሁኔታ በአስከፊ ሁኔታ መታሰራቸውን የእንግሊዝ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ፊሊፕ ሀሞንድ አውግዘዋል። የአቶ አንዳርጋቸው አያያዝ እና ደህንነት እንደሚያሳስበን በተደጋጋሚ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሃኖም ብንገልጽም ከቃል ያለፈ መልስ አለገኘንም፣ […]

ወጣቱ ፖለቲከኛ ዳዊት አስራደ የሚወዳቸውን ቤተሰቡንና ልጁን ትቶ ከሀገር መሰደዱ ተሰምቷል፡፡ ዳዊት ከ13ቱ የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ የስራ አስፈጻሚ እንዲሁም የብሄራዊ ምክር ቤት አባልና የአንድነትን የአምስት አመት ስትራቴጂክ እቅድም ከሌሎች የፓርቲው አመራሮች ጋር በመሆን የነደፈ ሙሉ ማንነቱን ለሀገር ትግል የሰጠ ቁርጥ ኢትዮጵያዊ ልጅ ነው፡፡ በ2002 ዓ.ም በአማራ ክልል ምርጫ ቅስቀሳ ላይ እያለ በመኪና ተገጭቶ ለ6 […]

ከሀገር ውጭም በስደት በሕውሓት ሰላዮች ክትትል ይደረግባቸው የነበሩ ኢትዮጵያውያኖች ከሰዳን ወደሊቢያ ገዞ ላይ እንዳሉ የሕውሓት ሰው ከሱዳን አቻው ጋር በመሆን በሱዳን ወታደራዊ ተሽከርካሪ ስደተኞቹ የተሳፈሩበትን ተሽከርካሪ በመግጨት አና እንዲገለበጥ በማድረግ አዳጋ ከደረሰባቸው መካከል የሥርዓቱ ሰው የነበረን ቁስለኛ ከሌሎች ጉዳት ከደረሰባቸው መካከል ፎቶ ከኪሱ በማውጣት ከፎቶው ካስተያየ በኋ በያዘው ሽጉጥ እንደረሸነው የአይን ምስክር ከሞት በተረፉት ሊጋለጥ […]

የተከሰሱት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እስር ተፈረደባቸው

መንግሥት በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ሁከት ፈጥረዋል ተብሎ ክስ የተመሠረተባቸው የሰማያዊ ፓርቲ አባላት፣ በሁለት ወራት እስራት እንዲቀጡ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቂርቆስ ምብድ ችሎት ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ሰጠ፡፡

በሊቢያ አይኤስ የተባለው ቡድን በኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን አሰቃቂ ግድያ ለማውገዝ፣ መንግሥት ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በመስቀል አደባባይ በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ረብሻ በመፍጠር፣ በመሳደብና ድንጋይ በመወርወር ሰላማዊ ሠልፉን አውከዋል ተብለው የተከሰሱት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤተልሔም አካለወርቅ መሆናቸው ይታወሳል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ ሊከላከሉ እንዳልቻሉ ገልጾ ጥፋተኛ ካላቸው በኋላ፣ የቅጣት አስተያየት ጠይቋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ቅጣቱ ከብዶ እንዲቀጡ አመልክቷል፡፡ ተከሳሾቹም የቤተሰብ አስተዳዳሪ መሆናቸውን፣ በተለይ ወይንሸት ሞላ ረብሻ ተፈጠረ በተባለበት ዕለት ጠዋት የታሰረች መሆኗንና የታሰረችበትን ፖሊስ ጣቢያ ገልጻ ቅጣቱ እንዲቀልላት ጠይቃለች፡፡

ፍርድ ቤት በሰጠው ፍርድ ቅጣቱ ከብዶ እንዲቀጡ የሚለው የዓቃቤ ሕግን የቅጣት ማክበጃ አስተያየት የተቀበለ ቢሆንም፣ በቡድን ስለመረበሻቸው ያቀረበው ማስረጃ እንደሌለ ገልጿል፡፡ በመሆኑም እያንዳንዳቸው እጃቸው ከተያዘበት ጀምሮ ያለው ጊዜ ተቆጥሮ፣ በሁለት ወራት እስራት እንዲቀጡ ፍርድ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾቹ ሁለት ወራት ከአንድ ቀን የታሰሩ በመሆናቸው በዕለቱ እንዲፈቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ፍርደኞቹ የማስፈቻ ትዕዛዝ ተዘጋጅቶላቸው ከማረሚያ ቤት የተፈቱት ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ቢሆንም፣ ከማረሚያ ቤት ሲወጡ ተይዘው በፀጥታ ኃይሎች ወደ ፖሊስ ጣቢያ መወሰዳቸውን ሰማያዊ ፓርቲ አስታውቋል፡፡ 

 

 

መድረክ የሟች አባላቱ ቁጥር አራት መድረሱን አስታወቀ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ግንቦት 16 ቀን 2007 ከተካሄደው አምስተኛውን ዙር ጠቅላላ ምርጫ በኋላ፣ ለሞት የተዳረጉ አባላቱ ቁጥር አራት መድረሱን አስታወቀ፡፡

በዚህም መሠረት ቀደም ሲል መሞታቸው ከተነገረው ሦስት የመድረክ አባላት በተጨማሪ፣ በደቡብ ክልል በሐድያ ዞን ሶሮ ወረዳ በዳና ቶራ ቀበሌ ነዋሪና የመድረክ አባል ድርጅት የሆነው የኢትዮጵያ ማኅበረ ዴሞክራሲ ደቡብ ሕዝቦች አንድነት ፓርቲ (ኢማዴ-ደሕአፓ) መሠረታዊ ኮሚቴ አባል የነበሩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ መገደላቸውን አስታውቋል፡፡ 

‹‹በ2007 ጠቅላላ ምርጫ በቅስቀሳ ላይ ተሰማርተው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ የቆዩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ፣ ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ በመኖሪያ መንደራቸው በተፈጸመባቸው ድብደባ ከተገደሉ በኋላ ወንዝ ውስጥ ተጥለው ተገኝተዋል፤›› ሲሉ የመድረክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንደሻው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በሥፍራው ካሉ የፓርቲው አደረጃጀቶች መረጃ እንደሚሰባሰብ የገለጹት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹መጀመርያ ቀን ላይ በአካባቢው ያሉ ፖሊሶችንና ሌሎች ካድሬዎችን ያካተተ አካል እየተንቀሳቀሱ፣ ሟችንና ሌሎች ለመድረክ የምርጫ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አባላትና ወጣቶችን ‹የማዳበሪያ ሒሳብ እንዳይከፈል ሕዝቡም በመንግሥት ላይ እንዲያምጽ ቅስቀሳ እያደረጋችሁ ነው፤› በማለት ሟችንና ወጣቶችን ለማስፈራራትና ለማሰር ሲንቀሳቀሱ ነበር፤›› በማለት፣ አጋጠመ ያሉትን አስረድተዋል፡፡

‹‹በተለይ ‹ማዳበሪያን በሚመለከት ዕዳው እንዳይከፈል ያደረጋችሁት እናንተ ናችሁ› ተብለው ፖሊስ ሊይዛቸው ሲል ሸሽተው ነበር፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ሟች ሸሽቶ ከቆየበት ሥፍራ ምሽት ላይ ወደ ቤቱ በሚያመራበት ወቅት ነው ግድያው የተፈጸመበት፤›› በማለት የፓርቲውን አባል የአሟሟት ሁኔታ አስረድተዋል፡፡

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ በሥፍራው የመድረክ ተወካይና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ግለሰብ ስለሁኔታው ለማጣራት ፖሊስ ጣቢያ ቢሄዱም፣ በፖሊስ ጣቢያው የዕለት ሁኔታ መመዝገቢያ ላይ የተመዘገበው ‹‹ሰክሮ ውኃ ውስጥ ወድቆ›› የሚል እንደሆነ መመልከታቸውን፣ አቶ ጥላሁን ከደረሳቸው ሪፖርት ለመረዳት መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹የምናካሂደው ሰላማዊ ትግል ብዙ መስዋዕነት እንደሚያስከፍለን እናውቃለን፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ቢሆንም ግን ሰላማዊውን ትግል አጠናክረን እንቀጥላለን፤›› በማለት አስተያየታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ሟች አቶ ብርሃኑ ኤረቦ የ40 ዓመት ጎልማሳና የአምስት ልጆች አባት እንደሆኑ መድረክ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ ላይ አስታውቋል፡፡

መድረክ ከምርጫው ዕለት ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ አቶ ጊዲሳ ጨመዳ፣ በምዕራብ  አርሲ ዞን ቆራ ወረዳ አቶ ገቢ ጥቤ፣ እንዲሁም በትግራይ ክልል ምዕራብ ትግራይ ዞን በማይካድራ ከተማ አቶ ታደሰ አብርሃ የተባሉ ዕጩዎቹ መገደላቸውን ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

 

ማዕድን ሚኒስቴር በአገሪቱ የሕግ አግባብ መሠረት ባለመሥራቱ፣ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ የማዕድን ማምረት ሥራ ላይ ከተሰማራው ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ማግኘት የሚገባውን ከ429 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማሳጣቱን የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታወቀ፡፡

የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በማዕድን ሚኒስቴር ላይ በ2006 ዓ.ም. አጠቃላይ የሥራ አፈጻጸም ላይ ባደረገው የክዋኔ ኦዲት ነው መንግሥት ከፍተኛ ገንዘብ ማጣቱን ያረጋገጠው፡፡ 

የማዕድን ሥራ አዋጅን በተመለከተ የወጣው የ1986 ዓ.ም. አዋጅ ከከበሩ ማዕድናት ሽያጭ አምስት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ እንደሚወስን፣ ባልከበሩ ማዕድናት ላይ ምንም የሚለው ነገር እንደሌለ የኦዲተሩ የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ያስረዳል፡፡

ይህ አዋጅ ግን በአዋጅ ቁጥር 678/2002 መሻሻሉን በዚህ መሠረትም የከበሩ ማዕድናት ላይ ስምንት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ መጣሉን፣ ያልከበሩ ማዕድናት ላይ ስድስት በመቶ መጣሉን ሪፖርቱ ያትታል፡፡

ይሁን እንጂ ማዕድን ሚኒስቴር ከሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኩባንያ የከበሩና በከፊል የከበሩ ማዕድናት ላይ አምስት በመቶ ብቻ ሮያሊቲ ክፍያ በመሰብሰቡ፣ ከ2004 ዓ.ም.  እስከ 2006 በጀት ዓመት ከሚድሮክ የወርቅ ሽያጭ መንግሥት ሊያገኝ የሚችለውን 252.9 ሚሊዮን ብር ማጣቱን፣ እንዲሁም ካልከበሩ ማዕድናት በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ብቻ 413,394 ብር ማጣቱን፣ በድምሩ በሁለት ዓመታት ውስጥ 253.37 ሚሊዮን ብር ለመንግሥት ገቢ መደረግ የነበረበት የሮያሊቲ ገንዘብ አለመሰብሰቡን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር በ2000 ዓ.ም. ማምረት የጀመረ ቢሆንም፣ ማዕድን ሚኒስቴር ግን ይህንን ተቋም በየወቅቱ እየተከታተለ ሒሳባቸውን እንዳልመረመረ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማረጋገጡን ይገልጻል፡፡ ይህም በመሆኑ በሮያሊቲ ሥሌቶች ላይ በሕግ ማሻሻያዎች የሚመጡ ለውጦችን በመከተል የመንግሥትን ገቢ ለማስገባት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እንዳልቻለ ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪም መንግሥት በሚድሮክ የወርቅ ማዕድን አክሲዮን ማኅበር ላይ ያለውን የነፃ ድርሻ በሕግ አግባብ ማስላት ባለመቻሉ፣ እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ 108.7 ሚሊዮን ብር እንዲሁም እስከ መጋቢት 2006 ዓ.ም. ድረስ 67.4 ሚሊዮን ብር በድምሩ 176.2 ሚሊዮን ብር አገሪቱ ማጣቷን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ይህ በመሆኑም የተፈጠረውን ስህተት በማረም መንግሥት ያጣው ገንዘብ እንዲመለስ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማዕድን ሚኒስቴሩን አሳስቧል፡፡

 

ከ17.7 ሚሊዮን ብር በላይ መመዝበሩ ተጠቅሷል

በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የደቡብ ሱዳን ሊሚትድ ጁባ ቅርንጫፍ ከ17.7 ሚሊዮን ብር በላይ በተጭበረበረ መንገድ ለግለሰቦች እንዲውል አድርገዋል ተብለው የሙስና ክስ የተመሠረተባቸው አምስት የባንኩ ሠራተኞች፣ ዋስትና

ተከልክለው ወደ ማረሚያ ቤት ወረዱ፡፡ አንዲት የቅርንጫፍ ባንኩ ከፍተኛ ኦዲተር በዋስ ተለቀቁ፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ክስ የመሠረተባቸው የባንኩ ሠራተኞች፣ የሒሳብ ሹም አቶ ረሚላ ለወይ ኡስማን፣ የደንበኞች ሥራ አስኪያጅ አቶ ፍፁም ብርሃን ዓለም ስምኦን፣ ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ሀብታሙ ዮሴፍ ማርዬ፣ ማኔጂንግ ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ሚካኤል ተክለ እግዚ ገብረ ማርያም፣ የንግድ አገልግሎት መኰንን አቶ ደስታው ፈንታሁን መንበር (ያልተያዙ)፣ ዋና ኦዲተር ወ/ሮ ሙሉሸዋ ክብረት፣ እንዲሁም አቶ መሐመድ ሁሴን ጣቢር (ያልተያዙ) እና አቶ ሁሴን ለወይ ኡስማን የተባሉ ግለሰቦች ናቸው፡፡ 

የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ ሲቴፕ ፎር ትሬድ ኤንድ ኢንቨስትመንት ካምፓኒ ሊሚትድ የተባለ ድርጅት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጁባ ቅርንጫፍ ደንበኛ ነው፡፡ በባንኩ በኩል 4,360,000 ዶላር ኤልሲ በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ባንክ ይፈቀድለታል፡፡ ዶላሩ የሚለቀቅለት በሦስት ጊዜ ክፍያዎች ነው፡፡ ክፍያው የሚፈጸመው ገንዘቡ ኬንያ ወደሚገኘው ስታንቢክ ባንክ ከተላለፈ በኋላ ነው፡፡ የመጀመርያው 1,453,33 ዶላር ተልኮለታል፡፡ ለድርጅቱ የሚላከው ዶላር ከደቡብ ሱዳን ፓውንድ ጋር ተመጣጣኝ የሆነና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ባንክ ካለው ሒሳብ ተቀንሶ መሆኑን ክሱ ያስረዳል፡፡

ነገር ግን አንደኛ ተከሳሽ አቶ ረሚላ ለድርጅቱ የተላከውን የገንዘብ መጠን መቀነስ ሲገባው ሳይቀንስ መቅረቱን ክሱ ያክላል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ ሒሳብ ሲሠራ (Reconciliation) ሳይቀነስ የቀረው ገንዘብ ተንጠልጣይ ሆኖ ሲያየው ማዕከላዊ ባንኩ እንዲቀንስ ማድረግ ቢገባውም አለማድረጉ ክሱ ጠቅሷል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ በሌሉበት ክሱ በተመሠረተባቸው አቶ መሐመድ ሁሴን ጣቢር ስም በ200 የደቡብ ሱዳን ፓውድ አካውንት እንዲከፍቱ ማድረጋቸውም ተጠቅሷል፡፡ በመቀጠልም በተለያዩ ጊዜያት በድምሩ 3,008,813 የደቡብ ሱዳን ፖውንድ የያዙ አራት ቼኮች ወደ  ኬንያ ንግድ ባንክ ለቼክ ማጣራት በማዕከላዊ ባንኩ በኩል ሲላኩ፣ የኬንያ ባንክ በግለሰቡ ገንዘብ እንደሌለው የገለጸ ቢሆንም አንደኛው ተከሳሽ ቼኮቹንና ተያያዥ ቅጾችን በማጥናት ግለሰቡ ገንዘብ ያለው ማስመሰሉ ክሱ ያብራራል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ የዴቢት ትኬት በማዘጋጀትና ከሁለተኛ ተከሳሽ ጋር አቶ ፍፁም ብርሃን ጋር በጣምራ ፈርመው የተንጠለጠለው ገንዘብ መሐመድ ሁሴን በተባለ ተከሳሽ ስም ወደ ተከፈተው ሒሳብ እንዲገባ በማድረግ በባንኩ ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ በአጠቃላይ ገንዘቡ በኢትዮጵያ ብር ሲሰላ 17,768,589 ብር መሆኑን፣ ተከሳሾቹ በሥልጣን ያላግባብ መጠቀም የሙስና ወንጀል ክስ እንደተመሠረተባቸው የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

ተጠርጣሪ ተከሳሾቹ ከላይ የተገለጸውን ገንዘብ በሕገወጥ መንገድ የተገኘ መሆኑን እያወቁ፣ በሐሰተኛ መንገድ በስድስተኛ ተከሳሽ አቶ መሐመድ ስም በተከፈተ ሒሳብ የተቀመጠውን ገንዘብ ከተለያዩ አካውንቶች የተላኩ በማስመሰልና ወደተለያዩ የባንክ ሒሳቦች አዘዋውረናል፡፡ የተለያዩ ተሽከርካሪዎችን፣ አንድ ባለሁለት መኝታ የኮንዶሚኒየም ቤት በመግዛት፣ በአጠቃላይ አንደኛ ተከሳሽና ስድስተኛ ተከሳሽ የአንደኛ ተከሳሽን ወንድም ሰባተኛ ተከሳሽ አቶ ሁሴን ለወይንን በመጠቀም፣ ገንዘቡን ማቀናነሳቸውንና በሕገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስለው በማቅረብ የሙስና ወንጀል መከሰሳቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሹ አቶ ፍፁም ብርሃን ዓለም የወንጀል ሕግ አንቀጽ 411 (2)ን በመተላለፍ የመንግሥትን ሥራ በማያመች አኳኋን በመምራት በሕጋዊ መንገድ ማግኘት ከሚገባቸው በላይ 6,620,600 ብር ይዘው መገኘታቸውንና ይኼም የሙስና ወንጀል መሆኑን ክሱ ይገልጻል፡፡ ሦስተኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ ዮሴፍም ማግኘት ከሚገባቸው በላይ 8,298,880 ብር ከሕጋዊ ገቢያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸውን፣ አራተኛም ተከሳሽ አቶ ሚካኤል ተክለ እግዚም 27,930,429 ብር ከሕጋዊ ገቢያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸው፣ አቶ ደስታው ፋንታሁንም 2,684,876 ብር ከሕጋዊ ገበያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸው፣ በፈጸሙት ምንጩ ያልታወቀ ንብረትና ገንዘብ ይዞ መገኘት የሙስና ወንጀል መከሰሳቸውን ክሱ ያብራራል፡፡

በቅርንጫፉ ዋና ኦዲተር የነበሩት ወ/ሮ ሙሉሸዋ ክብረት ሒሳቦችን በአግባቡ ባለመቆጣጠራቸውና የሥራ ኃላፊነትን ባለመወጣት የሚፈጸም የወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸዋል፡፡ ተጠርጣሪ ተከሳሾቹ ችሎት ቀርበው ክሱ ከተነበበላቸው በኋላ በጠበቆቻቸው አማካይነት ክሱ ዋስትና እንደማያስከለክል፣ ምክንያቱ ደግሞ አዲስ በወጣው የኮሚሽኑ አዋጅ መሠረት ዋስትና የሚከለክል አንቀጽ መሻሩን ጠቅሰው በዋስ እንዲለቀቁ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ የተጠቀሰው አንቀጽ ዋስትና እንደሚከለክልና በአዲሱ አዋጅ ዋስትናን የሚመለከተው አንቀጽ እንዳልተሰረዘ በመግለጽ ጥያቄውን ተቃውሟል፡፡ ፍርድ ቤቱ የደቂቃዎች ረፍት ወስዶ በሁለቱ ወገኖች ክርክር ላይ ከተወያየ በኋላ፣ በድጋሚ በመሰየም ከኦዲተር በስተቀር ሌሎቹን ተከሳሾች ዋስትና ከልክሏቸዋል፡፡ ኦዲተሯም ዋስትና ተፈቅዶላቸዋል፡፡ የክስ መቃወሚያ ለመስማት ለሐምሌ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

 

 

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም በደረሱት የአስተዳደራዊ በደል ጥቆማዎች ላይ ተመሥርቶ በሚያደርገው ምርመራ የመፍትሔ ሐሳቦችን ቢያቀርብም፣ አንዳንድ መሥሪያ ቤቶች እምቢተኝነት እያሳዩ መሆናቸውን አስታወቀ፡፡ ከእነዚህም መካከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትልቁን ድርሻ እንደሚይዝ ገለጸ፡፡

 

ዋና የሕዝብ እንባ ጠባቂዋ ወ/ሮ ፎዚያ አሚን የተቋማቸውን የአሥር ወራት የሥራ ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት፣ በአስተዳደር ጥፋት ምክንያት የደረሰ በደል እንዲታረም የተመርማሪ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎች ትብብርና ድጋፍ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የአስተዳደር በደል አቤቱታዎች ሲደርሱት አልያም በተደጋጋሚ ከሚደርሰው ጥቆማ በመነሳት የራሱን ምርመራ እንደሚያደርግ የገለጹት ወ/ሮ ፎዚያ፣ በምርመራው መሠረት የመፍትሔ ሐሳቦችን ለሚመለከታቸው ተቋማት እንደሚልክና የመፍትሔ ተቀባይነትም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡

ሆኖም የተወሰኑ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች በተቋሙ የምርመራ ውጤት ላይ ተንተርሶ በተላከላቸው የመፍትሔ ሐሳቦች መሠረት አለመፈጸም ወይም የማይፈጸሙበት በቂ ምክንያት ካላቸው ለተቋሙ ያለመግለጽና በምርመራ ሒደት አስፈላጊውን ትብብር ያለማሳየት እንቢተኝነት እንደሚታይ ገልጸዋል፡፡

ከእነዚህም ተቋማት መካከል በተደጋጋሚ ስሙ የተገለጸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው፡፡ ከአስተዳደሩ አካላት መካከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና ክፍለ ከተሞች ይገኙበታል፡፡

በተጨማሪም የኦሮሚያ የአርሲ ዞን አስተዳዳር ጽሕፈት ቤት፣ የምሥራቅ ሸዋ ዞን አስተዳዳር ጽሕፈት ቤት፣ የሐዋሳ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና በሐረሪ ክልል የፍትሕና የፀጥታ ጉዳይ ቢሮ በእነዚህ ችግሮች የተጠቁ መሆናቸውን ዋና እንባ ጠባቂዋ ወ/ሮ ፎዚያ ገልጸዋል፡፡

የተገለጹት ተቋማት በቀረበላቸው የመፍትሔ ሐሳቦች መሠረት የእርምት ዕርምጃ ባለመውሰዳቸው ልዩ ሪፖርት ለፓርላማው የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳዳር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በዝርዝር መላካቸውን የጠቀሱት ወ/ሮ ፎዚያ፣  ቋሚ ኮሚቴው ባደረገው ክትትል በደሎቹ በከፊል የታረሙ መሆኑን ነገር ግን ሙሉ በሙሉ አለመቀረፋቸውን ገልጸዋል፡፡

ራሱ ተቋሙ ወደ ፍርድ ቤት በመውሰድ ለምን እነዚህን ተቋማት እንደማያስቀጣ የተጠየቁት ዋና እንባ ጠባቂዋ፣ በአስተዳደራዊ በደል አቤቱታ ላይ ምርመራን መሠረት ያደረገ የመፍትሔ ሐሳብ አቤቱታ ለቀረበበት ተቋም የሚቀርብ መሆኑን ገልጸው፣ ተቋሙ በቂ ምክንያት ካለው ይኼንኑ ገልጾ የመፍትሔ ሐሳቡን ላለመተግር እንደሚችል በአዋጁ መደንገጉን ተናግረዋል፡፡

‹‹በቂ ምክንያት ካለው›› የሚለው ሐረግ ለትርጉም ክፍት በመሆኑ ዕርምጃ ለመውሰድ እንዳላስቻላቸው የገለጹት ወ/ሮ ፎዚያ፣ ይኼን ችግር ለመቅረፍ አዋጁን ለማሻሻል በዝግጅት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) መንግሥት ድጎማ  እንዲያደርግለት ያዘጋጀውን ፕሮፖዛል፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ሊያቀርብ ነው፡፡

ታኅሳስ 26 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትሩና በኢሠማኮ አመራሮች መካከል በተደረገ የምክክር መድረክ ላይ፣ ኢሠማኮ ለመንግሥት ይደረግልኝ ብሎ ያቀረበውን ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቃል አወንታዊ ምላሽ ሰጥተው እንደነበር ይታወሳል፡፡

 

በዚሁ ምላሽ መሠረት ኢሠማኮ የመንግሥትን ድጎማ እሻባቸዋለሁ ያላቸውን ጉዳዮች በዝርዝርና በፕሮፖዛል መልክ አዘጋጅቷል፡፡ ያስፈልገኛል ያለውንም የገንዘብ መጠን በመጥቀስ  ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር አቅርቦ ነበር፡፡

ይህንን ፕሮፖዛል ያቀረበው ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ቢሆንም፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ምንም ዓይነት ምላሽ ሳይሰጠው ቆይቶ ነበር፡፡ ቆይቶም ግን ኢሠማኮ ለሚኒስቴሩ ያቀረበው ጥያቄ መቅረብ ያለበት ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ነው የሚል ምላሽ ስለተሰጠው፣ ‹‹ድጎማ ይሰጠኝ›› የሚለውን ጥያቄውን በድጋሚ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ለማቅረብ እየተዘጋጀ መሆኑን፣ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግልን የፈለግነው ለግንዛቤ ማስጨበጫና ለአቅም ግንባታ ፕሮግራሞች ማስፈጸሚያ የሚውል ነው፤›› ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ይህንንም በፕሮፖዛላቸው ላይ ማስፈራቸውን ተናግረዋል፡፡

በተከታታይ በየዓመቱ የአሠሪና ሠራተኞችን ግንኙነት በሚመለከት የኢንዱስትሪ ሰላምን ለመፍጠር በሚያስችሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ ሁሉም ወገን መብትና ግዴታውን እንዲወጣ ለማድረግ ለሚያስፈልገው ወጪ መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግ በኢሠማኮ ተጠይቋል፡፡ ሥልጠናዎቹና የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞቹ በአሠሪና በሠራተኛ ዘንድ አሉ የሚባሉትን ችግሮች ለመፍታት፣ ሠራተኛውና አሠሪውን የሚመለከቱ ሕጎች ምን እንደሚመስሉ ለማሳየትና በዚሁ መሠረት ተፈጻሚ እንዲሆን ለማስቻል ጭምር ነው፡፡ ድጎማው ለተፈለገው ዓላማ ብቻ የሚውል ነው ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ከመንግሥት የሚገኘው የገንዘብ ድጎማ ለኢሠማኮ ውስጣዊ በጀት ወይም ለአስተዳደር ሥራ እንደማይውልና ደመወዝን ለመሰሉ ወጪዎች ማስፈጸሚያም እንደማይጠቀምበት ገልጸዋል፡፡

ኢሠማኮ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተመራው ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር አድርጎት በነበረው የምክክር መድረክ ላይ፣ ሊፈጸሙልኝ ይገባሉ ብሎ ካቀረባቸው ከ30 በላይ ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ ‹‹መንግሥት ኢሠማኮን ይደጉም›› የሚል ሲሆን፣ መንግሥትም ኢሠማኮን ለመደገፍ ፈቃደኝነቱን አሳይቷል፡፡

በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹ድጎማ የሚለው ቃል ጸያፍ ነው…በድጎማ ያደገ አገርና ድርጅት የለም፡፡ ሥራ ለመሥራት የገበያ ክፍተት ስላለ እንደ ልማታዊ መንግሥት ለዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አጋር ይሆናል ተብሎ እስከታመነ ድረስ በኢሠማኮ የተጠየቀውን እንሰጣለን፤›› ብለው፣ ‹‹ይህ ድጎማ ግን ለሽርሽር የምትጠቀሙበት አይደለም፤›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋቸው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ሠራተኞችን ማስጨብጨቡ ይታወሳል፡፡

በወቅቱ ሊፈቱልን ይገባል ተብለው ከኢሠማኮ ከቀረቡት ጥያቄዎች ውስጥ አብዛኞዎቹ አዎንታዊ ምላሽ እንዳገኙ የተነገረ ሲሆን፣ ከቀረጥ ነፃ ተሽከርካሪዎችም እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል፡፡ አሠሪዎች ለሠራተኞቻቸው የሚያቀርቡት ምግብ ታክስ እንዳይደረግ የሚለውም ጥያቄያቸው አወንታዊ ምላሽ እንዳገኘም ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

 

በአሁኑ ወቅት 85 በመቶ የተጠናቀቀው ከአዲስ አበባ-ጂቡቲ ድረስ እየተገነባ ያለው የባቡር መስመር በሚቀጥለው ዓመት አገልግሎት ይስጣል ተባለ፡፡

በሎስጂቲክስ ችግሮች ላይ መሠረታዊ ለውጥ ከማምጣቱም በላይ፣ ከውጭ ለሚገባ ከፍተኛ መጠን ያለው ማዳበሪያ ትራንስፖርት ተስፋ ተጥሎበታል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ግብዓት አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተወካይ አቶ በየነ ገብረ ሥላሴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ባቡሩ ሥራ የሚጀምር ከሆነ ማዳበሪያው ታሽጎ ወይም በብትን ይግባ የሚለው ይታያል፡፡ ነገር ግን ባቡሩ ሥራ ከጀመረ በብትን ማስገባቱ አዋጭ ይሆናል ሲሉ አቶ በየነ አስረድተዋል፡፡

ለሚቀጥለው ምርት ዘመን የሚፈለገውን ማዳበሪያ መጠን ለማወቅ ግብርና ሚኒስቴር ቅኝት እያደረገ መሆኑም ተገልጿል፡፡ ግብርና ሚኒስቴር ዘርፉ የሚፈለገውን የማዳበሪያ መጠንና ዓይነት ከክልሎች እየሰበሰበ ሲሆን፣ በይደር የሚቆየውን ማዳበሪያ መጠን በመገምገም ላይ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

የአገሪቱ ግብርና ዘርፍ የሚፈለገውን የማዳበሪያ መጠን እንደታወቀ፣ የግብርና ግብዓት አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ በጥቅምት 2008 ዓ.ም. ጨረታ አውጥቶ ግዥ እንደሚፈጽም ተጠቁሟል፡፡

ለ2007 ዓ.ም. ምርት ዘመን 894 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ዩርያና ኤንፒኤስ ማዳበሪያዎች ግዥ ተፈጽሞ፣ አብዛኛው አገር ውስጥ መግባቱ ይታወሳል፡፡ አገር ውስጥ የገባው ማዳበሪያ በኩንታል 1,200 ብር አካባቢ በመሸጥ ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

ነገር ግን በ2007 ዓ.ም. ግዥ ከተፈጸመው ማዳበሪያ ውስጥ አንድ መርከብ ማዳበሪያ በአሁኑ ወቅት በጂቡቲ ወደብ በመራገፍ ላይ ይገኛል፡፡ አቶ በየነ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ግብርና ሚኒስቴር አገሪቱ የምትፈልገውን የማዳበሪያ መጠንና ዓይነት እንዳሳወቃቸው ግዥ ለመፈጸም ወደ ገበያ ይወጣሉ፡፡

የግብርና ሚኒስቴር ግብርና ግብዓት ዳይሬክተር አቶ ተሾመ ላቀው በበኩላቸው፣ ክልሎች የማዳበሪያ ፍላጎታቸውን በነሐሴ ወር እንደሚያሳውቁና በጥቅምት ወር ወደ ግዥ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

በዚህ የምርት ዘመን ግዥ የተፈጸመው 894 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ ሲሆን፣ አንዱ ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ ከ412 ዶላር እስከ 480 ዶላር ግዥ ተፈጽሟል፡፡ በምርት ዘመኑ ለማዳበሪያ ዘርፍ አስቸጋሪ ጉዳይ የነበረው የትራንስፖርት ጉዳይ ሲሆን፣ ይህም የሆነው ማዳበሪያን በዝቅተኛ ዋጋ ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ሲባል በትራንስፖርት ሒሳብ ላይ ተመን በመውጣቱ ነበር፡፡

ይህም የትራንስፖርት ድርጅቶችን ትኩረት መሳብ ባለመቻሉና በወቅቱ በርካታ ዕቃዎች ጂቡቲ ወደብ ደርሰው የነበረ በመሆኑ፣ ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ ለማጓጓዝ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡

አቶ በየነ እንዳሉት፣ በሚቀጥለው ዓመት ይህንን ችግር ለመፍታት ከወዲሁ ከባህር ትራንስፖርትና ከሎጂስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ጋር ንግግር ይጀመራል፡፡ ከአዲስ አበባ ጂቡቲ ድረስ በሚገነባው የባቡር መስመር ችግሩ ሊቀረፍ እንደሚችል አቶ በየነ ያላቸውን እምነት ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የዓለም አቀፍ የማዳበሪያ ዋጋም በዚህ የምርት ዘመን ከተገዛበት ዋጋ ቅናሽ ይኖረዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የሚናገሩት አቶ በየነ፣ በሚቀጥለው ምርት ዘመን ለአርሶ አደሩ የሚቀርበው ማዳበሪያ የዋጋ ቅናሽ ሊኖረው ይችላል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ዘርፍ የሚፈልገው ማዳበሪያ መጠን እያደገ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ አፈሩ የሚፈልገው ማዳበሪያ ዓይነትም ተለይቶ እንደታወቀ ተገልጿል፡፡ በግብርና ዘርፍ ውስጥ ብዙም  የማይታወቀው ኤንፒኤስ ማዳበሪያ፣ የአገሪቱን ግብርና የተቀላቀለ በመሆኑ በአገሪቱ አምስት ማዳበሪያ ፋብሪካዎችም አፈሩ የሚፈልገውን ማዳበሪያ በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

 

ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ምርጫውን ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን ምርጫ ቦርድ አረጋገጠ

‹‹መድረክና ሰማያዊ ፓርቲዎች ሁለተኛና ሦስተኛ ሆነዋል›› ፕሮፌሰር መርጋ በቃና

-የጊምቦ ገዋታ የምርጫ ውጤት አልተካተተም

በመላው ኢትዮጵያ (ከጊምቦ ገዋታ ምርጫ ጣቢያ በስተቀር) ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የተካሄደውን የሕዝብ ተወካዮችና የክልል ምክር ቤቶች አገራዊ ምርጫ ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን፣

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በሒልተን ሆቴል ይፋ አደረገ፡፡

የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና እንደገለጹት፣ ቦርዱ በአዋጅ ቁጥር 532/99 አንቀጽ 77 መሠረት አጠቃላይ የምርጫውን ውጤት ይፋ ያደርጋል፡፡ በመሆኑም ለአምስተኛው አገራዊ ምርጫ 36,851,461 ሕዝብ በመራጭነት ተመዝግቦ፣ 34,351,444 ሕዝብ ድምፁን ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 334 ወንዶችና 212 ሴቶች በዕጩነት አቅርበው አሸናፊ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ምክር ቤቱ ካለው 547 መቀመጫዎች 546ቱን ሲያሸንፉ፣ ላለፉት አምስት ዓመታት ብቸኛው የግል የፓርላማ አባል የነበሩት ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስና የኢሕአዴግ ዕጩ ዶ/ር መብራቱ ገብረ ማርያም (የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት) የሚወዳደሩበት የቦንጋ ጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል ውጤት  ይፋ ባለመደረጉ፣ ከተገለጸው ውጤት ጋር አለመካተቱን ሰብሳቢው ተናግረዋል፡፡

ለክልል ምክር ቤቶች ኢሕአዴግና አጋሮቹ፣ 1187 ወንዶችና 800 ሴቶች በድምሩ 1,987 አባላት በዕጩነት አቅርበው ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን ፕሮፌሰሩ አክለዋል፡፡

ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 52 የፖለቲካና ዘጠኝ የግል ዕጩዎች ለ547 መቀመጫዎች የተወዳደሩ ቢሆንም፣ ኢሕአዴግ በአምስት ክልሎች ማለትም በአማራ፣ በትግራይ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በሐረሪ፣ በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች 27,347,332 ድምፅ በማግኘት 500 መቀመጫዎችን ያለምንም ተቀናቃኝ ማሸነፉን ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡

ለሁለቱ ምክር ቤቶች 40,536,607 የድምፅ መስጫ ወረቀቶች መቅረቡን የገለጹት ፕሮፌሰሩ፣ 1,130,390 ድምፅ መስጫ ወረቀቶች ዋጋ አልባ መሆናቸውንና 520,379 ድምፅ መስጫዎች መበላሸታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምርጫ ውድድሩ መድረክና ሰማያዊ ፓርቲዎች ሁለተኛና ሦስተኛ መውጣታቸውን የገለጹት ፕሮፌሰር መርጋ፣ የምክር ቤቶቹን መቀመጫዎች የሚያስገኝ ድምፅ ባለማግኘታቸው ተሸናፊ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡ ቦርዱ የሕዝብ ድምፅ ማስከበር እንዳለበት የተናገሩት ሰብሳቢው፣ ይኽንኑ ተግባራዊ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡ በደቡብ ክልል የጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል የምርጫ ውጤት ለቦርዱ መድረሱን ጠቁመው፣ ቦርዱ ውጤቱን ባለማፅደቁ በዕለቱ በገለጹት ውጤት ላይ አለመካተቱን፣ ነገር ግን  በቅርቡ ፀድቆ በቦርዱ ድረ ገጽ ይፋ እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡

ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. በደቡብ ክልል በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ በጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል በተካሄደው ምርጫ፣ የኢሕአዴግ ዕጩ ዶ/ር መብራቱ ገብረ ማርያም የግል ዕጩውን ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስን በሰፊ ውጤት ማሸነፋቸውን ከምርጫ ጣቢያዎቹ ከተገኘው መረጃ መረጋገጡን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

 

የትራፊክ መጨናነቅን ለመቀነስ አዲስ አበባ እስከ አዳማ የተገነባው የፍጥነት መንገድ አካል የሆኑ ሁለት መንገዶች በከፊል ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ሊሆኑ ነው፡፡

ከአቃቂ ለቡና ከአቃቂ የረር በመገንባት ላይ ያሉት መንገዶች አንደኛው መስመራቸው ለትራፊክ ክፍት እንዲሆን፣ ግንባታቸው በፍጥነት እንዲካሄድ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡

ሁለቱ መንገዶች ግንባታቸው በየካቲት 2008 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ ቢታቀድም፣ በአካባቢው እየተፈጠረ ያለው የትራፊክ መጨናነቅ በጣም እየጨመረ በመምጣቱ ትራንስፖርት ሚኒስቴር በሰጠው መመርያ፣ አንደኛው ረድፍ በአፋጣኝ ተገንብቶ ለትራፊክ ክፍት እንዲሆን ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡

በዚህ መሠረት የቻይናው ግዙፍ የኮንስትራክሽን ኩባንያ ሲሲሲሲ ግንባታው በማገባዳደድ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት እንደሚደረግ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጠን ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ሳምሶን ወንድሙ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የፍጥነት መንገዱ መጨረሻ ከሆነው አቃቂ ተነስቶ ለቡ ድረስ ያለው 13.6 ኪሎ ሜትር እና ከአቃቂ ተነስቶ አይሲቲ ፓርክ (የረር ጎሮ) ድረስ የሚገነቡት መንገዶች ናቸው ለትራፊክ ክፍት የሚሆኑት፡፡

እነዚህ መንገዶች በአጠቃላይ ስድስት መኪኖችን በአንድ ጊዜ የሚያስተላልፉ ሲሆን፣ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት የሚሆነው አንደኛው ረድፍ ሦስት መኪኖችን በአንድ ጊዜ ያስተላልፋል ተብሏል፡፡ በአጠቃላይ ሁለቱ የመንገድ ፕሮጀክቶች 4.6 ቢሊዮን ብር ወጪ የሚደረግባቸው ሲሆኑ፣ ከአጠቃላይ ወጪ 75 በመቶ የቻይና ኤግዚም ባንክ ቀሪውን 25 በመቶ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ይሸፍናሉ፡፡

የመንገዶቹ ግንባታ ባለፈው 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ነው የተጀመረው፡፡ በሁለት ዓመት ከስምንት ወር ይጠናቀቃል ተብሏል፡፡ ነገር ግን አንዱ ረድፍ የግድ ማለቅ አለበት በመባሉ ግንባታው እየተፋጠነ በመሆኑ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት ይሆናል፡፡

እነዚህ ሁለት መንገዶች ከአዲስ አበባ-አዳማ ድረስ የተገነባው ግዙፍ የፍጥነት መንገድ አካል ናቸው፡፡ የአዲስ – አዳማ የፍጥነት መንገድ 84.6 ኪሎ ሜትር ርዝመት ሲኖረው  12.2 ቢሊዮን ብር ወጥቶበታል፡፡ ሁለቱ መንገዶች እንደተጠናቀቁ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ከቃሊቲ እስከ አቃቂ ድረስ ያለውን መንገድ ደረጃ የሚያሻሽል መሆኑ ታውቋል፡፡

ይኼ መንገድ ብቸኛው የአገሪቱ ወጪና ገቢ ንግድ የሚከናወንበት በመሆኑ ተለዋጭ መንገድ ሳይገነባ የመንገዱን ደረጃው ማሻሻል አይቻልም ተብሎ ቆይቷል፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት የፍጥነት መንገዱ በሁለት አቅጣጫዎች ወደ አዲስ አበባ ከተማ በመዘርጋቱ፣ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ወደ ግንባታ ይገባል በማለት ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ፍቃዱ ኃይሌ አገር ውስጥ ባለመኖራቸው አስተያየታቸውን ማካተት ሳይቻል ቀርቷል፡፡

 

ትውልደ ኢትዮጵያዊው ገጣሚና ጸሐፊ ተውኔት የማንቸስተር ዩኒቨርሲቲ ቻንስለር ሆነ

በእንግሊዝ ማንችስተር ዩኒቨርሲቲ ለቻንስለርነት ከተወዳደሩ ሦስት ግለሰቦች መካከል ትውልደ ኢትዮጵያዊው ገጣሚና ጸሐፈ ተውኔት ለምን ሲሳይ አብላጫውን ድምፅ በማግኘት አሸነፈ፡፡

ለምን በወድድሩ የተሳተፉትን የሙዚቃ ባለሙያውን ሰር ማርክ ኤልደርና የቀድሞውን የእንግሊዝ ፖለቲከኛ ሎርድ ፒተር ማንዴልሰንን ሰፊ በሆነ የድምፅ ብልጫ አሸንፏል፡፡

ለምን ውድድሩን ያሸነፈው 7,131 የማንቸስተር ዩኒቨርሲቲ ሠራተኞችና የቀድሞ ተማሪዎችን ድምፅ በማግኘት ሲሆን፣ ሰር ማርክ ኤልደር 5,483 ድምፅ በማስመዝገብ ሁለተኛ ሆነዋል፡፡ እንዲሁም ፖለቲከኛው ሎርድ ፒተር 5,269 ድምፅ በማግኘት ሦስተኛ ሆነዋል፡፡

ለምን ከምርጫው በኋላ የዩኒቨርሲቲው ቻንስለር ለመሆን ያበቃውን ድምፅ የሰጡትን መራጮች አመስግኗል፡፡ ከነሐሴ አንድ ጀምሮ በሥልጣን ላይ ያሉትን ቶም ብሎክሳምን ተክቶ ለሰባት ዓመታት እንደሚሠራ ታውቋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ዴም ናንሲም ዩኒቨርሲቲውን በማስተዋወቅ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡ 

ገጣሚና ጸሐፊ ተውኔት ለምን ሲሳይ እ.ኤ.አ. በ1967 በዊጋን ከተማ ከኢትዮጵያዊ ቤተሰቦች የተወደለ ሲሆን፣ ከወላጆቹ ዘንድ ለማደግ አልታደለም ነበር፡፡ እስከ 12 ዓመቱም እንግሊዛዊ አሳዳጊዎቹ ዘንድ ቆይቷል፡፡ በኋላም በአካባቢው በሚገኝ ሕፃናት ማሳደጊያ ዕድሜው 17 እስኪሆን ቆይቷል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1988 በ21 ዓመቱ የግጥም መድበል አሳትሟል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1995 ‹ኢንተርናል ፍላይት› የሚባል በቢቢሲ ዘጋቢ ፊልም አዘጋጅቶ ለዕይታ አብቅቷል፡፡ ሌሎች በርካታ ስኬቶችም ተቀዳጅቷል፡፡

 

አለም ዝም ያለው, ታላላቅ ሀያላን ሀገራት ሁሉ ፀጥ ብለው ተመልካች የሁኑበት አረመኔያዊው እውነተኛው ትርኢት በጭራሽ አላባራም. እንዲያውም ብሶበታል. ሶሪያ ደበነች, ኢራቅን ፈጁት, ሊቢያ ን አናወዟት, ግብፆችን አረዱ, ኢትዮጵያዊንኑ ወንድሞቻችን ደገሙ. ኮሪያ, አሜሪካ, ኤርትራ ብቻ ያልነካኩት የለም ግን ዝም ተብለዋል. ሀይ ባይ አልተገኘም. አንድ ቡድን አለምን ሲያስጨነቅ አለም መሪዎች ያጣች ይመስላል. ነገሩ ግራ የገባ ነው. ልምምዳቸው […]

አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ አሁንም ስቃይ ላይ መሆናቸው በኬንያ ወያነ የላካቸው ደህንነቶች ከተለያዩ የመገናኛ መሳሪያዎች ጋር በቁጥጥር ስር መዋላቸው የአቢሲኒያ ባንክ ሰራተኞች የተቃዋሚ ድርጅት ደጋፊ ናቸው ተብሎ በኢሕ አዴግ ባለስልጣናት መፈረጃቸው በሁመራ አሸባሪዎች ገቡ በሚል ሽፋን ህወሃት ህዝቡን እያሸበረ መሆኑን ተነገረ የሰማያዊ ፓርቲ የምስራቅ ጎጃም ዞን ፀኃፊ ሳሙኤል አወቀ በወያኔ ጭፍሮች ባሳለፍነው ሳምንት መገደሉ ተሰምታልFiled under: NEWS […]

መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስረው ሰኔ 15/2007 ዓ.ም በቄራ ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት እንዲፈቱ የተወሰነላቸው ወንይሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤትሄልየም አካለ ወርቅ ዛሬ ሰኔ 16/2007 ከእስር ተፈትተው ሲወጡ በፖሊስና ደህንነቶች ታፍነው ታስረዋል፡፡ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ታስረው የነበሩት ኤርሚያስ ፀጋዬና ዳንኤል ተስፋዬ ከእስር ከተፈቱ በኋላ የ6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ፖሊሶች […]

ዛሬ ቤተ እስራኤላዊያን ሰላማዊ ስልፍ  በቴል አቪብ ያደርጋሉ ምክንያቱም ባለፍው ቤተ እስራኤላዊ በፖሊስ ተመቶ ነበር ፖሊሱ እስር ቤት መግባት አለበት ብለው ሲጠይቁ የተሰጠው መልስ መጀመሪያ የተማታው ቤተ እስራኤላዊ ነው ፖሊሱ አይድለም የሚል ነበር ይህን ያስቆጣቸው ቤተ እስራኤላዊያን ዝም ብለው አልተመለከቱም በዛሬው እለት በአደባባይ ይወጣሉ አንድ ፍክራ አላቸው ይህም አንድ ሰው ለሁሉም ነው ሁሉም ለአንድ ሰው […]

የኢትዮጵያ መንግስት ያሰማራቸው ሰላዮች በህዝብ ጥቆማ ቢያዙም መለቀቃቸው ህዝቡን አስቆጥቷል ትናንት ረፋድ አካባቢ በናይሮቢ ነዋሪ የሆኑ ሶስት የፖለቲካ ስደተኛ ኢትዮጵያዊያን በኬንያ ፖሊስ ለጥያቄ እንደሚፈለጉ ተነግሯቸው ሲወሰዱ በዛ ያሉ ሰዎች ተፈላጊዎቹን በመከተል ፖሊስ ጣብያ ድረስ በማምራት የተያዙት እንዲለቀቁ አልያም ተላልፈው ለኢትዮጰያ መንግስት እንዳይሰጡ በመጠየቅ ምላሽ ካላገኙ ፖሊስ ጣብያውን እንደማይለቁ በማስረዳታቸው የፖሊስ ጣብያው ኃላፊዎች ሰዎቹን አሳልፈው እንደማይሰጡ […]

በኦሮሚያ ክልል፤ ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ድምፃችን ተሰረቀ በማለት ወደ ዩኒቨርሲቲ አስተዳዳሪዎች አቤቱታቸው ስላቀረቡ ብቻ በስርዓቱ ታጣቂዎች ጥይት እንደተተኮሰባቸው ተገለፀ። በምንጮቻችን መረጃ መሰረት በመቱ ዩኒቨርሲቲ የተካሄደውን ምርጫ አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ለተቃዋሚ ድርጅቶች መምረጣቸውን የተረዱት የስርዓቱ ካድሬዎች የምርጫው ኮረጆ ሰርቀው በመቀየር ኢህአዴግ 1568 አብላጫ በማግኘት አሸንፈዋል በማለት ግንቦት 17/ 2007 ዓ/ም ይፋ ያደረጉትን ውጤት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ስላልተቀበሉት ዓመፅ […]

ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሠራተኞች መልቀቅ ችግር ሆኖብኛል አለ

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በክፍያና በሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ማነስ ምክንያት፣ በጣም በርካታ ሙያተኞች መልቀቃቸውንና በምትካቸውም ብቁ ሙያተኛ ለመቅጠር ክፍያው ሳቢ አለመሆኑን ገለጸ፡፡ 

የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ጥሩነህ ዜና ያለፉትን አሥራ አንድ ወራት የኮሚሽኑን የዕቅድ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት ነው ይኼንን ችግር ያነሱት፡፡

እንደ ኮሚሽነሩ ገለጻ፣ 12 ወንዶችና ሰባት ሴቶች በድምሩ 19 ሠራተኞች ሥራቸውን ለቀዋል፡፡ መሥሪያ ቤቱ ሠራተኞች መልቀቅና በምትካቸው መቅጠር ባለመቻሉ ባለፉት 11 ወራት ያጋጠመው ችግር በማለት ለፓርላማው አባላት አስረድተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ለኮሚሽኑ ዕቅድ ማስፈጸሚያ ከመንግሥት የተፈቀደው የመደበኛ በጀት አነስተኛ ከመሆኑም በላይ፣ በየወሩ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የሚለቀቀው ወይም አንድ-አሥራ-ሁለተኛ የሚባለው አሠራር፣ በተለይም በኮሚሽኑ የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች አሠራር ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ ሌላው ኮሚሽኑን ያጋጠመው ተፅዕኖ እንደሆነ ኮሚሽነሩ  አስረድተዋል፡፡

በበጀት ዓመቱ ያጋጠሙት እነዚህ ችግሮች ቢኖሩም፣ ኮሚሽኑ ያከናወናቸው ተግባራት መኖራቸውን ኮሚሽነሩ አስረድተዋል፡፡ በዚህም ረገድ በአጠቃላይ የ2007 ዓ.ም. አምስተኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ ሕገ መንግሥቱን፣ የምርጫ ሕጎችንና ዓለም አቀፍ መሥፈርቶችን መሠረት ባደረገ ሁኔታ፣ የመምረጥና የመመረጥ መብቶችን ጨምሮ የዜጎች ሰብዓዊ መብቶችን ባከበረ መንገድ እንዲፈጸም ክትትል ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

የሴቶችና የሕፃናት መብትን ለማስጠበቅ እንዲቻል፣ በተለይም የመብት ጥሰት መንስዔ የሆኑትን ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና የግል ጥቃቶች ለመከላከል ብሎም ለማስወገድ የተጀመሩ ሕዝባዊ ንቅናቄዎችና መድረኮች እንዲጠናከሩ ኮሚሽኑ ያደረገው ድጋፍ እንዲሁ በበጀት ዓመቱ ከተከናወኑ ጠንካራ ክንውኖች መሀል የሚጠቀሱ መሆናቸውን ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል፡፡

ላለፉት አምስት ዓመታት ኮሚሽኑን በኮሚሽነርነት ሲያገለግሉ የነበሩት አባላት በአዲስ ለመተካት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኅብረተሰቡ የዕጩዎች ጥቆማ እንዲያደርግ ያስነገረ ሲሆን፣ በዚህም መሠረት በአዲሱ የፓርላማው የመጀመሪያ ዓመት  አዲስ ኮሚሽነር የሚመረጥ በመሆኑ፣ ይህ ሪፖርት በአምባሳደር ጥሩነህ አማካይነት የቀረበ የመጨረሻው ነው፡፡

 

የእነ አቶ መላኩ ፈንታ ክስ ለሁለተኛ ጊዜ የሕገ መንግሥት ትርጉም ጥያቄ አስነሳ

በቀድሞው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር በእነ አቶ መላኩ ፈንታ መዝገብ በከባድ ሙስና የተከሰሱ ነጋዴዎችና የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የጉምሩክ አዋጅ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይገባል ወይስ አይገባም በሚለው

ጉዳይ ላይ ለመወሰን፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ መንግሥት ትርጉም እንዲሰጥ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 15ኛ ወንጀል ችሎት ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉዳዩን መራለት፡፡

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክሱን መሠረት ያደረገው በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 411 (የመንግሥት ሥራን ለማያመች አኳኋን መምራት) እና በተሻሻለው የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 622/2001 ላይ ነው፡፡ ይሁንና አዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 859/2006 በቀድሞው ሕግ በወንጀልነት የተፈረጁ ድርጊቶችን የሚሽር ነው፡፡ ተከሳሾቹም ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡት ጥያቄ በኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 22(2) ላይ የወንጀል ክስ የቀረበበት ድርጊት ከተፈጸመ በኋላ የወጣ ሕግ ለተከሳሹ ጠቃሚ ሆኖ ከተገኘ፣ ከድርጊቱ በኋላ የወጣው ሕግ ተፈጻሚ እንደሚሆን ስለሚደነግግና የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 5(3)ም በተመሳሳይ ይኼንኑ የሚደነግግ በመሆኑ፣ በአዲሱ ሕግ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከተሻሩት አንቀጾች ነፃ እንዲወጡ ነው፡፡

ይኼን ጥያቄ ካቀረቡት ተከሳሾቹ መካከል አቶ መላኩ ፈንታ፣ አቶ ገብረ ዋህድ ወልደ ጊዮርጊስ (የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር)፣ አቶ ነጋ ገብረ እግዚአብሔር (የነፃ ትሬዲንግ ባለቤት)፣ አቶ ስማቸው ከበደ (የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባለቤት) እና ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ (የአዲስ ካርዲያክ ሆስፒታል መሥራችና ባለድርሻ) ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ፍቅር ማሩ የተከሰሱት ከመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመመሳጠር የሕክምና ዕቃዎችን በሕገወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ አስገብተዋል ተብለው ነው፡፡ በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ይኼ ድርጊት በገንዘብ የሚያስቀጣ እንጂ፣ የወንጀል ድርጊት ባለመሆኑ ነፃ መውጣት እንዳለባቸው ተከራክረዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ግን ድርጊቱ ኮንትሮባንድ በመሆኑ ይኼ ድርጊት ግለሰቡን በወንጀል ከመጠየቅ አያድናቸውም ሲል ተከራክሯል፡፡ በተጨማሪም የወንጀል  ሕግ አንቀጽ 411 አሁንም እንዳልተሻረ አስታውሷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተከራካሪ ወገኖችን ክርክር ከሰማ በኋላ አዲሱ አዋጅ ተከሳሾቹን ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለውን ጭብጥ መርምሯል፡፡ ፍርድ ቤቱ በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ በቀድሞው አዋጅ ወንጀል የነበሩ ድርጊቶች መሻራቸውን ማረጋጡን ገልጿል፡፡ ይሁንና በአዲሱ አዋጅ አንቀጽ 182 ላይ ‹‹በሌሎች ሕጎች የተደነገገው እንደተጠበቀ ሆኖ ይኼ አዋጅ ከፀናበት ቀን በፊት የተጀመሩ ጉዳዮች በነበረው ሕግ መሠረት ፍፃሜ ያኛሉ፤›› ተብሎ መደንገጉ ልዩ ሁኔታን እንደሚፈጥር አስገንዝቧል፡፡ የወንጀል ሕጉ ጠቅላላ ሕግ በመሆኑና የጉምሩክ አዋጅ ደግሞ ልዩ ሕግ በመሆኑ፣ በመርህ ደረጃ ልዩ ሕግ ከጠቅላላ ሕግ ቅድሚያ ተሰጥቶት ተግባራዊ እንደሚሆን አመልክቷል፡፡ ነገር ግን ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ሕግ በሕግነት ፀንቶ የማይቆም በመሆኑ፣ አዲሱ ሕግ ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚጣጣም ስለመሆኑ መመርመር እንደሚያስፈልግ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡

በፍርድ ቤቱ ዕይታ የአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ አንቀጽ 182 በሕገ መንግሥቱ ከተቀመጡት አንቀጽ 9፣ 13 (ሕገ መንግሥቱ የበላይ ሕግ ስለመሆኑና ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚፃረር ማንኛውም ሕግና ውሳኔ እንደማይፀና ይደነግጋሉ) እና 22 ጋር የሚጣጣም ባይሆንም፣ ሕገ መንግሥቱን የመተርጎም ሥልጣን የሌለው በመሆኑ የዚሁ ሥልጣን ባለቤት የሆነው የፌዴሬሽን ምክር ቤት ጉዳዩን መርምሮ ሕገ መንግሥቱን በመተርጎም፣ ውሳኔውን ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. እንዲያቀርብ መርቶታል፡፡ 

ይኼው ክስ ከዚህ ቀደም ባስነሳው ሌላ ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የከፍተኛ የፌዴራል መንግሥት ባለሥልጣናት ጉዳይ በጠቅላይ ፍርድ ቤት የመጀመርያ ደረጃ ሥልጣን እንዲታይ የሚደነግገው አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀጽ 8(1)፣ በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠውን ይግባኝ የመጠየቅ መብት የሚጥስ ነው ተብሎ እንዲሻር ማድረጉ ይታወሳል፡፡

 

የቻይና መንግሥት ከፍተኛ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ የኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ትኩረት እንዲደረግ፣ ዝቅተኛና መካከለኛ ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ያደረጉ ፋብሪካዎች ደግሞ ተነቅለው ወደ አፍሪካ እንዲሄዱ ማዘዙ ተሰማ፡፡

ከአፍሪካ አገሮች በተለይ ግብፅና ኢትዮጵያ ተመርጠዋል፡፡ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ ዕድገት ይበጃሉ ያላቸውን ፋብሪካዎች ለመቀበል፣ ከቻይና ናሽናል ዴቨሎፕመንትና ሪፎርም ኮሚሽን ጋር ለመደራደር ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የቻይና መንግሥት ዝቅተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ከአገር ወጥተው እንዲሠሩ ውሳኔ ያሳለፈው፣ አገሪቱ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ያላትን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ከፍተኛ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ ፋብሪካዎች ላይ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል በማለቱ ነው ተብሏል፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪም በቻይና የአገልግሎት ዘርፍን ለማሳደግና ከዚህ ቀደም ርካሽ የነበረው የሰው ኃይል በአሁኑ ጊዜ እየተወደደ በመምጣቱ፣ ፋብሪካዎቹ ከአገር ወጥተው በማደግ ላይ ባሉት ኢትዮጵያና ግብፅ እንዲተከሉ መመርያ ማስተላለፉ ተነግሯል፡፡

ይህንን እንደ መልካም አጋጣሚ የተመለከተው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ ለአገሪቱ ዕድገት ወሳኝ የሚባሉ ፋብሪካዎችን በመምረጥና የቻይና መንግሥት ሊያቀርብ ስለሚችለው የፋይናንስ ሁኔታ ድርድር እንዲያደርግ፣ ኃላፊነቱን ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር መስጠቱ ታውቋል፡፡

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሱፍያን አህመድ የሚመሩት የልዑካን ቡድን በቅርቡ ወደ ቻይና ተጉዞ፣ ከቻይና ብሔራዊ ዴቨሎፕመንትና ሪፎርም ኮሚሽን ኃላፊዎች ጋር የመጀርያውን ድርድር ማካሄድ እንደሚጀምር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ 

የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከግብርና በማላቀቅ በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ መሠረት ላይ ለማሳረፍ ያቀደው የኢትዮጵያ መንግሥት በተለይ ለጨርቃ ጨርቅ፣ ለቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ ለብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ፣ ለስኳር ልማትና ለኬሚካል ኢንዱስትሪ ልማት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቷል፡፡

ይህንን ዕቅድ ለማሳካትም በዶ/ር አርከበ እቁባይ የሚመራው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን፣ በአሥር ቢሊዮን ዶላር ወጪ በተለያዩ ከተሞች የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በማቋቋም ላይ ይገኛል፡፡

ወደ ኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ እንዲቀላቀሉ የሚመረጡት የቻይና ፋብሪካዎች በእነዚህ የኢንዱስትሪ ዞኖች ውስጥ ወይም ራሳቸው በሚያቋቁሟቸው የኢንዱስትሪ ዞኖች ውስጥ ፋብሪካዎቻቸውን እንዲተክሉ እንደሚደረግ፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ዘርፍ ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶችን ለማምረት አመቺ መሆኑን ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ መንግሥት ኢንቨስትመንት በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ተዋናዮችን ለማረበታታት ያወጣቸው በርካታ ሕጎችና ማበረታቻዎች፣ እንዲሁም በአገሪቱ ያለው የሰው ኃይል አገሪቱን ተመራጭ ማድረጉን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

  

 

በቴክኒክና በንግድ ሥራ የሠለጠኑ 63 ሴቶች ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቁ፡፡ በሥልጠናው በወተትና የሥጋ ምርት አቅርቦት፣ እንዲሁም የቁም ከብት ንግድ ላይ ክህሎት የሚያሳድግ ግንዛቤ ማግኘታቸውን በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

ሥልጠናውን ያዘጋጀው የአሜሪካ መንግሥት በዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲው (USAID) ሲሆን፣ በ2004 ዓ.ም. በሴቶች ላይ በተደረገ ጥናት በወተት ምርት፣ በእንስሳት ዕርባታ፣ በአመራር ዕውቀት፣ በንግድ ሥራ አገልግሎቶች ተደራሽነት፣ ውሳኔ በመስጠት፣ በስኬታማ የንግድ ሥራ ዕቅድ አዘገጃጀት ረገድ የታዩትን ክፍተቶች ለመሙላት ነው ተብሏል፡፡ 

የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ኤጀንሲ ‹‹ወደፊትን መመገብ›› በተሰኘ ፕሮግራሙ በግብርና ዕድገት ፕሮግራም የእንስሳት ገበያ ልማትና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ በሚያስችል አቅም መመረቅ በተሰኙ መርሐ ግብሮች፣ በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ሥልጠና ሰጥቷቸዋል፡፡ በሥልጠናው የተካተቱት ሴቶች የሥራ ፈጠራ አቅም እንዳላቸው የታመነባቸው መሆናቸው በመግለጫው ተመልክቷል፡፡ ሴቶቹ በአስተዳደርና በሥራ አመራር ክህሎት ሥልጠና የተሰጣቸው ሲሆን፣ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያግዝ የንግድ ሥራ ዕቅድ በመንደፍ ረገድም የቴክኒክ ዕውቀት ማግኘታቸው ተገልጿል፡፡

ሠልጣኞቹ ከአማራ፣ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል እንዲሁም ከትግራይ ክልል የተውጣጡ ናቸው፡፡ በቆይታቸው ያገኙትን ክህሎት በአካባቢያቸው ለሚገኙ ሴቶችም እንደሚያካፍሉ ይጠበቃል፡፡

ሴቶች በእንስሳት ዕርባታና በእንስሳት ምርት አያያዝ የሚጫወቱትን ሚና ማሳደግ ለቤተሰብም ሆነ በአገር ደረጃ ከፍ ያለ ጠቀሜታ አለው ያሉት የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ ተወካይ ካለን ሒዩስ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት በንግድ ሥራ አስተዳደርና በአመራር ላይ ያተኮረው ሥልጠና፣ በእንስሳት ዕርባታ ዕምቅ አቅም ያላቸው አርዓያ ሴቶች ላይ ማተኮሩ፣ በዘርፉ የመሪነቱን ሚና እንዲጫወቱ ያግዛቸዋል፡፡ በሥልጠናው ያልተካተቱ ሴቶችም በሠልጣኞቹ አማካይነት ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል፡፡ 

 

መንግሥት የፓርቲዎቹን መግለጫ ውድቅ አድርጓል

በአንድ ቀን ልዩነት የአረና/መድረክ እና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በተለያዩ ሥፍራዎች ተገድለው በመገኘታቸው ምክንያት ሰማያዊ ፓርቲና አረና/መድረክ በመንግሥት ላይ ወቀሳ አቀረቡ፡፡

ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. በአማራ ክልል በምሥራቅ ጎጃም ዞን በደብረ ማርቆስ ከተማ አቶ ሳሙኤል አወቀ የተባሉ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ ሲገደሉ፣ በማግሥቱ አቶ ታደስ አብረሃ የተባሉ የአረና/መድረክ አባል በትግራይ ክልል ምዕራብ ዞን ማይካድራ ከተማ  መገደላቸውን ሁለቱም ፓርቲዎች አስታውቀዋል፡፡

አረና/መድረክ ባወጣው መግለጫ አባሉ በምዕራብ ትግራይ ዞን የድርጅቱ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው በ2007 ምርጫ ወቅት፣ የፓርቲውን ሥራ በማደራጀትና በማንቀሳቀስ ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ የቆዩ መሆናቸውን፣ ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት ለጊዜው ባልታወቁና ቤታቸው በመጡ ሦስት ሰዎች ግድያ እንደተፈጸመባቸው አስታውቋል፡፡

ፓርቲው የገዳዮቹን ማንነት አለመታወቁን በጠቆመበት መግለጫ፣ ሟች አባሉ ከግድያው ቀደም ብሎ በመንግሥት የፀጥታ ሠራተኞች ወከባና ማስፈራርያ ይደርስባቸው እንደነበር ጠቁሟል፡፡

‹‹ለጉዳተኛው የሕክምና ዕርዳታ እንዲደረግላቸው ለማስተባበርና ወንጀለኞችም ለመከታተልና ለማስያዝ የተደረገው ሙከራ በፖሊሶች አለመተባበር›› ሳይሳካ መቅረቱን በመግለጫው አረና/መድረክ አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይም ሰማያዊ ፓርቲ አቶ ሳሙኤል የተባሉ አባሉ ከመገደላቸው በፊት፣ በደኅንነት ሠራተኞችና በአካባቢው ሹሞች የግድያ ማስፈራርያ ይደርሳቸው እንደበር ገልጿል፡፡

የምሥራቅ ጎጃም ዞን ፖሊስ መምርያ በበኩሉ አቶ ሳሙኤል በሁለት ግለሰቦች መገደላቸውን ገልጾ፣ አንደኛው ተጠርጣሪ በቁጥጥር ሥር ውሎ ሲመረመር ግድያውን መፈጸሙን ማመኑን አስታውቋል፡፡

ነገር ግን የፖሊስን መግለጫ ሙሉ በመሉ ውድቅ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ‹‹የሰማዕታት ደም ይጮሃል፣ ይጣራል›› በሚል ርዕስ ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹ይህ ሥርዓት በሕግም፣ በሞራልም ኢትዮጵያን የማስተዳዳር ብቃት የለውም፡፡ ወንጀለኞችን ለፍርድ ይቅረቡ እያልን አናላዝንም፣ ወንጀለኞቹ የመንግሥት አካላት ናቸውና፤›› ሲል መንግሥትን ምንም ዓይነት ፍትሕ እንደማይጠብቅም ገልጿል፡፡

እንዲሁም አረና/መድረክ በበኩሉ በትግራይ ክልል ከ17 በላይ አባላት ጨምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራና በደቡብ ክልሎች በአባላት ላይ እስራት፣ ግርፋትና ግድያ እየተፈጸመባቸው መሆኑን በመግለጫው አስፍሯል፡፡

መንግሥት በበኩሉ ክሶቹን ውድቅ በማድረግ ተገደሉ በተባሉት ሰዎች እጁ እንደሌለበት ገልጾ፣ ትችቶቹ ሁሉ እውነትነት የሌላቸው መሆኑን አስታውቋል፡፡

በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሽመልስ ከማል፣ ‹‹ሁለቱም የተቃዋሚዎች አባላት በግለሰቦች መገደላቸውንና ጉዳዮችን ይዞ ለፍርድ ለማቅረብ ፖሊስ ምርመራውን ቀጥሏል፡፡ መንግሥት እንደሚያምነው የሁለቱ ዜጎች መገደል ምንም ዓይነት ፖለቲካዊ ይዘት የለውም፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በተለይ የሰማያዊ ፓርቲ አባል ግድያ አሳዛኝ እንደሆነ፣ ሟች ከቀድሞ ደንበኞቹ ጋር በተፈጠረው አለመግባባት መገደሉን ፖሊስ አረጋግጧል  ካሉ በኋላ፣ አቶ ታደሰ በማይታወቁ ሰዎች ከመገደላቸውና ፖሊስ ምርመራ እያደረገ መሆኑን ከማወቃቸው ውጪ፣ ገና መረጃው እንዳልደረሳቸው አቶ ሽመልስ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የአረና/መድረክ አባልን ግድያ በተመለከተ የትግራይ ክልል የፀጥታና የደኅንነት ቢሮን ምላሽ ለማግኘት ሪፖርተር ተደጋጋሚ ጥረት ቢያደርግም፣ ኃላፊዎችን በስብሰባ ምክንያት ለማግኘት ባለመቻሉ አስተያየታቸውን ማካተት አልተቻለም፡፡ 

 

የ120 ሚሊዮን ዶላር የኃይል ማስተላለፊያ መስመር ግንባታ ስምምነት ተፈረመ

ኢትዮጵያና ኬንያን በኤሌክትሪክ ኃይል ለማገናኘት፣ በኢትዮጵያ በኩል የ433 ኪሎ ሜትር ኃይል ማስተላለፊያ መስመር መገንባት የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ፡፡ ስምምነቱ ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል

አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀና ግንባታውን ለማካሄድ የተመረጠው የቻይናው ስቴት ግሪድ እህት ኩባንያ ሲኢቲ ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ሚስተር ቸንግ ዊ በሸራተን አዲስ ተፈራርመዋል፡፡ የኃይል መስመሩ አንደኛው ኮንትራት በ120 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የሚገነባ ሲሆን፣ ወጪው በአፍሪካ ልማት ባንክ ይሸፈናል ተብሏል፡፡ ግንባታው ከወላይታ ሶዶ ተነስቶ ኬንያ ድንበር ሞያሌ ላይ የሚቆም ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ያለውን 612 ኪሎ ሜትር የኃይል መስመር ኬንያ ትገነባለች፡፡ ኢትዮጵያ 400 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለኬንያ ለመሸጥ ስምምነት ያረገች በመሆኗ፣ አንዱን ኪሎ ዋት በሰባት የአሜሪካ ሳንቲም ለመሸጥ ስምምነት ተደርጓል፡፡

የቻይናው ኩባንያ የፈረመው በኢትዮጵያ በኩል ከሚገነቡት ሁለት ኮንትራክተሮች መካከል አንዱ ሲሆን፣ በቅርቡ አንደኛው ኮንትራት ይፈረማል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በኬንያ በኩል የሚገነባው የኃይል መስመር በሦስት ኮንትራቶች የተከፈለ ነው፡፡ ግንባታውን ለማካሄድ አሸናፊ ከሆኑ የህንድ ኩባንያዎች ጋር በቅርቡ ስምምነት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህ ግንባታ በ26 ወራት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሏል፡፡ የቻይናው ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንትም ግንባታው በተያዘለት ጊዜ ገደብ እንደሚጠናቀቅ ቃል ገብተዋል፡፡ በምሥሉ ላይ ኢንጂነር አዜብ አስናቀና የቻይናው ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ቸንግ ዊ ስምምነቱን ከተፈራረሙ በኋላ፡፡

 

የመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ባለፉት 11 ወራት አርባ ያህል ከፍተኛ ኪሳራ ሊያስከትሉ የሚችሉ የሳይበር (ኮምፒዩተርን መሠረት ያደረጉ) ጥቃቶችን ማምከኑን፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታወቀ፡፡

ኤጀንሲው ከተቋቋመ በርካታ ዓመታት ቢያልፉም፣ እንደ አዲስ በተነደፈው አሠራር መሠረት ለመጀመርያ ጊዜ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምክር ቤቱ አቅርቧል፡፡

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል ተክለ ብርሃን ወልደ አረጋይ እንደገለጹት፣ የአገሪቱን ቁልፍ መሠረተ ልማቶች ለማጥቃት የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች ነበሩ፡፡

‹‹ወደ አገራችን የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች በርካታና ብዙ መልክ  ያላቸው ናቸው፤›› ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ‹‹አንዳንድ የጥቃት ዓይነቶች አገራችንን በተለየ ሁኔታ ዒላማ ያላደረጉ ነገር ግን ማንኛውም ተጋላጭ መሠረተ ልማትን የሚያጠቁ ሲሆን፣ እንደዚህ ዓይነት ጥቃቶች በየቀኑ ከዚህ አልፎም በየሰዓቱ የሚሠራጩ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

ሌሎች ሆን ተብሎ የኢትዮጵያን የሳይበር መሠረተ ልማት ለማጥቃት የሚለቀቁ ቫይረሶች መኖራቸውን የገለጹት ሜጀር ጄኔራል ተክለ ብርሃን፣ ወደ አርባ የሚጠጉ በአጠቃላይ መሠረተ ልማቱንና የተወሰኑ ቁልፍ ተቋማትን ዒላማ ያደረጉ ከፍተኛ ኪሳራ ሊያደርሱ የነበሩ የሳይበር ጥቃቶችን ለማምከን መቻሉን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ጥቃቱ ቢደርስ ኖሮ ሊያስከትል የነበረው ኪሳራ በጣም ትልቅ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ ከዚህ ውጪ የሳይበር ጥቃቶቹ በየትኞቹ ቁልፍ ተቋማት ላይ እንደተሠነዘሩ፣ እንዲሁም ከየት አካባቢ እንደሆነ አልገለጹም፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪ በቴሌኮም ማጭበርበር ተግባር ላይ የተሰማሩ 55 ተጠርጣሪዎች በሕግ ቁጥጥር ሥር መዋላቸውን፣ ለዚህ የወንጀል ተግባር ሲጠቀሙባቸው የነበሩ ወደ 170 የተራቀቁና ዘመናዊ ሕገወጥ የቴሌኮም መሣሪያዎች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡ ግለሰቦቹ በቴሌኮም ወንጀል ተሰማርተው በነበረበት ወቅት 700 ሚሊዮን ብር ኪሣራ በኢትዮ ቴሌኮም ላይ ማድረሳቸውንም ተናግረዋል፡፡

ኤጀንሲው የተሰጠውን ተልዕኮ በተቀናጀና በተጠናከረ መንገድ ለመወጣት እንዲችል ቀደም ሲል የተጀመረውን በዘርፉ ያሉትን የሕግ፣ የፖሊሲና የስታንዳርድ ክፍተቶች በመለየት ክፍተቶችን ለመዝጋት እየሠራ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡

ከእነዚህም መካከል የሳይበር ወንጀል ሕግ ረቂቅ ማዘጋጀት አንዱ ሲሆን፣ በ2005 ዓ.ም. ለካቢኔ ቀርቦ የነበረ ነው፡፡ ረቂቅ ሕጉ ከፍትሕ ሚኒስቴር ጋር በመሆን እንደገና እንዲታይ በመወሰኑ በድጋሚ በመታየት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

  

እስራኤላዊው ምሁር ከስደት ተመላሽ ወገኖች አክራሪነት እንዳላጠላባቸው እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል አሉ

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥርጣሬውን አጣጥሏል

በዓለም አቀፍ የፀረ ሽብር ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪና በእስራኤል መንግሥት የዲፕሎማሲና የስትራቴጂ ተዛምዶ ማዕከል አማካሪ የሆኑት ዶ/ር ዮናታን ፋይን፣ ኢትዮጵያ ከስደት የምትመልሳቸው ዜጐቿ ከአክራሪነት ጥላ የራቁ መሆናቸውን

ማረጋገጥ እንደሚገባት አሳሰቡ፡፡ የደኅንነትና ዓለም አቀፍ ጥናት ምሁሩ ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት ከየመን፣ ከሊቢያና ከሌሎችም የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ወደ አገር ቤት በሚመለሱ ዜጐች ላይ መንግሥት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡

ዓለም አቀፍ የሽብር ቡድኖችና ጽንፈኛ እምነትን የሚያራምዱ ግለሰቦችና ድርጅቶች በሞሉባቸው የመካከለኛው ምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ አገሮች በብዛት የሚገኙት ኢትዮጵያውያን፣ በአንድም ሆነ በሌላ አጋጣሚ በእነዚህ አካላት ተፅዕኖ ሥር ወድቀው ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡ ይህም እነዚህ ወገኖች ወደ አገራቸው ገብተው ከሚገጥሙዋቸው የመልሶ መዋሀድ ተግዳሮቶች ጋር ተዳምሮ ላልተፈለገ የባህርይ ለውጥ ሊዳርጋቸው እንደሚችል ምሁሩ ገልጸዋል፡፡

ይህ ጥርጣሬ ለምን እንደገባቸው ተጠይቀው የመለሱት ምሁሩ፣ በተለያዩ የዓለም አገሮች የተደረጉ ጥናቶች የሚያሳዩት መረን ላወጣ አፈንጋጭነትና አክራሪነት እርሾ የሚሆኑት ባህርያት በሆነ ወቅት ወደ አገር ቤት ተመልሰው መኖር በሚጀምሩ ዜጎች ምክንያት የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ በተለይ በርካታ ዜጐቿን በስደት የምታጣው አፍሪካ ዜጎቿ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች ከሚገጥማቸው የኑሮ ውጣ ውረድ ጋር ተዳምሮ፣ ለአዳዲስና የኑሮ ሁኔታን ሊቀይሩ ይችላሉ ለተባሉ አስተሳሰቦች በቀላሉ የመንበርከክ ዕድል እንዳላቸውም ገልጸዋል፡፡ በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በምዕራብና በመካከለኛው አፍሪካ የሚገኙ በርካታ ዜጐች በእነዚህ አዳዲስ አስተሳሰቦች በመማረካቸው ምክንያት ወደ አገራቸው ሲመለሱም ይህንኑ አቋማቸውን እንደሚገፉበት ምሁሩ ያስረዳሉ፡፡

እስራኤላዊው ምሁር እስካሁን ድረስ በኢትዮጵያ የሚታየው ሁኔታ በዚህ ደረጃ የሚጠቀስ አለመሆኑን፣ የሕዝቡ የረጅም ዘመናት ተቻችሎ የመኖር ልማድ ለዚህ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን እንደሚያምኑ ገልጸው፣ ነገር ግን ይህ ሁኔታ በተለያዩ የውጭ ተፅዕኖዎችና አካባቢያዊ ሁኔታዎች ሊሸረሸር እንደሚችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ለዚህም ኢትዮጵያ የምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋትና ለአደገኛ ቡድኖች አመቺ ሥፍራ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ 

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ፣ የምሁሩ አስተያየት ምንም መሠረት የለውም ባይባልም ዓለም አቀፋዊ ገጽታን የተላበሰ መሆኑን በመጠቆም፣ ለጊዜው ግን ሥጋትን የሚያጭር አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህንን ጉዳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በቀጥታ ባይመለከተውም፣ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ተገቢውን ሥራ እንደሚያከናውን እገምታለሁ፡፡ በእኛ በኩል ከየትም አገር የሚመጣ ዜጋ በኤምባሲዎችና በቆንስላዎች አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ ሲያሟላ እናስተናግዳለን፤›› ሲሉ አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀዳሚ ዓላማም የዜጐችን ማንነትና ምንነት ማጥናት ሳይሆን፣ የነፍስ አድን ተግባሩን በማቀላጠፉ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ 

እንደ ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አይኦኤም መረጃ፣ በየመን ብቻ ከ50 ሺሕ በላይ ኢትዮጵያውያን መኖራቸው ሲታወቅ እስካሁን ድረስ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸው ታውቋል፡፡ በሊቢያ የሚገኙ ዜጐችም በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆናቸውንም የድርጅቱና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጀመረውን የነፍስ አድን ዘመቻ አጠናክሮ እንደሚቀጥልበት፣ በየትኛውም አገር የሚገኝ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ሊጠቀምበት የሚችል ዕድል መሆኑንም አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በእስራኤል የሚገኙ ቤተ እስራኤላውያንን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ምንም የቀረበ ጥያቄ አለመኖሩን፣ ጥያቄው ከቀረበ ግን እነሱንም ለመርዳት መንግሥት ዝግጁ መሆኑን አቶ ተወልደ አስታውቀዋል፡፡

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን ለሪፖርተር ያጋሩት እስራኤላዊው ምሁር ዶ/ር ዮናታን፣ ኢትዮጵያውያኑ ቤተ እስራኤላውያን በእስራኤል እየገጠማቸው ያለው ፈተና አሳሳቢ መሆኑን፣ በአንዳንድ ምግባረ ብልሹ የፀጥታ ኃይሎች የሚፈጸመውን ጥቃትም አጥብቀው የሚቃወሙ በርካታ እስራኤላውያን መኖራቸውን በመጠቆም፣ የቤተ እስራኤላውያኑ የመብት ጥያቄዎች ሁሉ ምላሽ ሊያገኙ እንደሚገባቸው አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህ የዘር መድልኦ ዛሬም ድረስ በአሜሪካና በሌሎችም ያደጉ አገሮች የሚስተዋል በመሆኑ፣ የእስራኤልን ሁኔታ አዲስ አያደርገውም፡፡ ከዚህ በፊት ሩሲያውያንን ጨምሮ ሌሎችም ትውልደ እስራኤላውያን በተመሳሳይ ችግር ውስጥ አልፈው እዚህ በመድረሳቸው፣ ቤተ እስራኤላውያኑም በቅርብ ጊዜ ችግራቸው እንደሚፈታ እገምታለሁ፤›› በማለት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተደጋጋሚ የሚከሰተውን የቤተ እስራኤላውያን ቁጣና የእስራኤል ባለሥልጣናትን ዘገምተኛ የመፍትሔ ዕርምጃ ገልጸውታል፡፡     

 

ባራክ ኦባማ ኢትዮጵያን ሊጎበኙ ነው

የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ በሐምሌ ወር አጋማሽ ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናትና ከአፍሪካ ኅብረት አመራሮች ጋር እንደሚመክሩ፣ ዋይት ሀውስ አስታወቀ፡፡

በሥራ ላይ ያለ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ኢትዮጵያን ጎብኝቶ አያውቅም፡፡

የበርካታ አገሮች መሪዎች ይታደሙታል ተብሎ የሚጠበቀው ከሐምሌ 5 እስከ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚካሄደው ሦስተኛው ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ጉባዔ ባራክ ኦባማ ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ይሁንና የዋይት ሀውስ መግለጫ ፕሬዚዳንቱ ለዚሁ ጉባዔ ስለመምጣታቸው የሚያወሳው ነገር የለም፡፡ 

ጉባዔው በመስከረም ወር 2008 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቀውን የምዕተ ዓመቱ የልማት ግብን ይተካል የተባለለት ዘላቂ የልማት ግቦችን ለመተግበር የሚያስችሉ የፋይናንስ ምንጮች ላይ ይመክራል፡፡ ይህንኑ ጉባዔ ለመከታተል ከ5,000 በላይ የአገር መሪዎች፣ ፖለቲከኞች፣ የግል ተቋማት፣ የሲቪል ማኅበራትና የሚዲያ ተወካዮች አዲስ አበባ እንደሚመጡ ይጠበቃል፡፡

የዋይት ሀውስ የፕሬስ ጉዳዮች ኃላፊ ጆሽ ኧርነስት የኦባማ የኢትዮጵያ ጉብኝት አሜሪካ ከአፍሪካ አገሮች ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከርና በአፍሪካ ኢንቨስት የማድረግ ቁርጠኝነት ያላት መሆኑን ለማሳየት ያለመ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮችና ዜጎች ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲያመጡ፣ ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲገቡና የደኅንነት ይዞታቸውን እንዲያጠናክሩ አሜሪካ የምታደርገው ጥረት አካል እንደሚሆንም ገልጸዋል፡፡ 

ፕሬዚዳንት ኦባማ በኬንያ የሚካሄደውን ዓለም አቀፍ የሥራ ፈጠራ ጉባዔ ከተከታተሉ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ ታውቋል፡፡ የባራክ ኦባማ አባት ኬንያዊ ቢሆኑም ይህ ጉዟቸው እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚደረግ ነው፡፡   

 

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ምስማር ለማምረት ከሚያገለግለው ስታፋ ብረት (ዋየር ሮድ) ለዓመታት የቆየውን ታሪፍ ከለላ እንዲነሳ ማድረጉ ውዝግብ አስነሳ፡፡

የታሪፍ ከለላው መነሳት በኢትዮጵያ የሚካሄደውን የምስማር ንግድ፣ አንድ ኩባንያ ብቻ በሞኖፖል እንዲቆጣጠር በር ከፍቷል የሚሉ ምስማር አምራች ኩባንያዎች ጉዳዩን ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ወስደውታል፡፡

ስታፋ ብረት ላይ የታሪፍ ከለላ በመነሳቱ ቅሬታቸውን ካቀረቡት 76 ፋብሪካዎች መካከል 46 የሚሆኑት ትላልቅ የምስማር ፋብሪካዎች፣ በአዲስ አበባና በዙሪያዋ በሚገኘው ኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ ይገኛሉ፡፡ ከምስማር አምራቾች በተጨማሪ በታሪፍ ከለላ መነሳቱ በትግራይ፣ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ለውኃና ለአፈር ጥበቃ የሚያገለግለው ጋብዮን (በሽቦ የተሠራ መረብ) የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ይገኙበታል፡፡ 

ሚኒስቴሩ ሚያዚያ 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ባስተላለፈው መመርያ የስታፋ ብረት ከውጭ ሲገባ፣ 20 በመቶ የጉምሩክ ታክስና አምስት በመቶ ዊዝ ሆልዲንግ ታክስ እንዲከፈል አድርጓል፡፡ ሚኒስቴሩ እዚህ ውሳኔ አይ የደረሰው በአገር ውስጥ ስታፋ ብረት በብቸኝነት የሚያመርተው ስቲሊ አርኤምአይ ኩባንያ ለመጥቀም ሲሆን፣ የአገር ውስጥ ምስማር አምራቾች ስታፋ ብረት ከስቲሊ አርኤምአይ በመግዛት ሥራቸውን እንዲያካሂዱ ለማድረግ የታሪፍ ከለላውን አንስቷል፡፡

ቅሬታ አቅራቢ ምስማር አምራቾች የተላለፈው መመርያ አንዱን ወገን ማለትም ጥሬ ዕቃውን ማምረት ለጀመረው ስቲሊ አርኤምአይ ኩባንያ ለመደገፍ የወጣ እንጂ ፍትሐዊነት የሌለው አሠራር ነው በሚል ይተቻሉ፡፡

“በስታፋ ብረት ላይ የሁለተኛ ደረጃ ታሪፍ ከለላ መነሳቱን ይበልጥ አስቸጋሪ ያደረገው የስታፋ ብረት አገር ውስጥ ማምረት የጀመረው እስቲሊ አርኤምአይ እህት ኩባንያ የሆነው አስመን ላለፉት 15 ዓመታት የምስማር ገበያን 65 በመቶ ድርሻ የያዘ በመሆኑ ነው፤” በማለት ቅሬት አቅራቢ ኩባንያዎች ለሚመለከታቸው የመንግሥት ተቋማት ባስገቡት ደብዳቤ ተገልጿል፡፡

ስቲሊ አርኤምአይ እና እህት ኩባንያው አስመን የስታፋ ብረትና የምስማር ዋጋ በሞኖፖል ለመወሰን እንዲችሉ ከፍተኛ አቅም ይሰጣል በማለት፣ የሚኒስቴሩን መመርያ አግባብነት የሌለው እንደሆነ የቅሬታ አቅራቢዎቹ ደብዳቤ ጨምሮ ያስረዳል፡፡ የስቲሊ ኤምአርአይ የኦፕሬሽንና ፖሊሲ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተፈራ ለማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ስታፋ የሚሸጥበት ዋጋ ለሁሉም አምራች ኩባንያዎችም ሆነ ለእህት ኩባንያ አንድ ነው በማለት ምሳሌ ጠቅሰው አስረድተዋል፡፡ ደብዳቤው ሚኒስቴሩ መመርያውን ካስተላለፈ ከጥቂት ወራት በኋላ ጉዳዩን የሚያጠና ኮሚቴ ተቋቁሞ እንደነበርም ያስታውሳል፡፡ ኮሚቴውን የንግድ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አህመድ ኑሩ የመሩ ሲሆን፣ ኮሚቴው ባካሄደው ጥናትም ስቲሊ አርኤምአይ የስታፋ ብረት በበቂ መጠንና በሚፈለገው ጥናት እያመረተ መሆኑን፣ የቀረበው የሞኖፖሊ ሥጋትም “በአሠራር ማስወገድ እንደሚቻል” በመጥቀስ የታሪፍ ማሻሻያው ተገቢ መሆኑን አስተያየት ሰጥቷል፡፡

የብረት አምራቾች ግን ይህንን ሐሳብ በፍፁም አልተቀበሉትም፡፡ የታሪፍ ከለላው የተነሳው ስቲሊ አርኤምአይን ሆን ብሎ ለመጥቀም ነው በማለት መከራከርያቸውን ያቀርባሉ፡፡ ይህ ውሳኔ የኢንቨስትመንት ፈቃድና የኢንቨስትመንት ማበረታቻ በተሰጣቸው በርካታ አምራቾች ላይ ሊያስከትል የሚችለው ተፅዕኖ አልታየም፡፡ ስቲሊ አርኤምአይ ከሚያመርታቸው ልዩ ልዩ ምርቶች አንዱን በመነጠልና በአንዱ ምርት ላይ ያነጣጠረና በርካታ አምራቾችን ከገበያ የሚያስወጣ ነው በማለት ቅሬታ አቅራቢዎቹ ይናገራሉ፡፡ 

የበለጠ እሴት ጭማሪ ያለውና ከፍተኛ የሰው ኃይል የሚቀጥረው የምስማር ፋብሪካ ከውጭ በሚያስገባው የስታፋ ብረት ላይ የተነሳው የታሪፍ ከለላ በጥልቀት ያልታየና በጥናት ላይ ያልተመሠረተ ነው በማለት፣ ቅሬታቸውን በጽሑፍ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አቅርበዋል፡፡ 

የምስማር ፋብሪካዎቹ እንደሚሉት የታሪፍ ከለላ በመነሳቱ ስታፋ ብረት ከውጭ በማስገባት ምስማር ማምረት አዋጭ አይደለም፡፡ ከስቲሊ አርኤምአይ ስታፋ ብረት ገዝቶ ምስማር ማምረትም አዋጭ አይደለም ይላሉ፡፡

አዋጭ ያልሆነበት ምክንያት ሲያብራሩ፣ በተወሰደው ዕርምጃ የጥሬ ዕቃ መግዣና የምርቱ የመሸጫ ዋጋ በዋናነት የሚወሰኑት ስቲሊ አርኤምአይ እና እህት ኩባንያው አስመን ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ለብዙ ዓመታት በሥራ ላይ የቆዩ የምስማር አምራች ኩባንያዎች፣ ‹‹ከሥራ እንድንወጣ እያደረገን ነው›› በማለት ቅሬታቸውን አስተጋብተዋል፡፡ “በተቀመጠው አቅጣጫ ጥሬ ዕቃ ከስቲሊ በመግዛት ሥራችንን እናስቀጥል ብለው የጀመሩ አንዳንድ የምስማር ፋብሪካዎችም ቢሆኑ፣ በዋናነት በስቲሊና በአስመን እየተፈጠረ ባለው የዋጋ መዛባት ሥራውን በተገቢው መንገድ ለመቀጠል ተቸግረዋል፤” በማለት ቅሬታ አቅራቢዎቹ በደብዳቤ ይገልጻል፡፡ 

በአቶ አህመድ የሚመራው ኮሚቴ በምስማር አምራቾቹ የቀረበው የሞኖፖሊ ሥጋት በአሠራር ማስወገድ እንደሚቻል የገለጸ ቢሆንም፣ የሞኖፖሊ ሥጋት እንዴት እንደሚወገድ የሚገልጽ የአሠራር ዘዴ ግን አያይዞ አላቀረበም በማለትም ይወቅሳሉ፡፡ 

“በስታፋ አምራቹ ስቲሊ አርኤምአይ እና በምስማር ምርት ትልቁን ድርሻ በሚያመርተው እህት ኩባንያው አስመን የሞኖፖል አሠራሮች ለማስወገድ የሚያስችል አሠራር ተቀይሶ ተግባራዊ ማድረግ ሲገባ፣ አንድ ወገን ብቻ በማየት የተወሰነው ውሳኔ በዋጋ ላይ እንደተጠበቀው ከፍተኛ ችግር ያስከተለ መሆኑንና እንዲያውም አንዳንድ ፋብሪካዎች ከነጭራሱ እስከ መዘጋት ደርሰዋል፤” በማለት ቅሬታ አቅራቢ የምስማር ፋብሪካዎች ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባቀረቡት ቅሬታ ይገልጻሉ፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ቅሬታ አቅራቢዎቹ እንደሚሉት ስቲሊ አርኤምአይ በስታፋ ብረት የነበረው ከለላ ሲነሳ፣ የምስማር ፋብሪካዎች የስታፋ ብረት ከውጭ ሲያስገቡና የምስማር ነጋዴዎች ያለቀለት ምስማር ከውጭ ሲያስገቡ የሚከፍሉት የጉምሩክ ቀረጥና ዊዝ ሆልዲንግ ታክስ ተመሳሳይ ስለሚሆን፣ ስታፋ ብረት ከውጭ አስገብቶ ምስማር ከማምረት ይልቅ ያለቀለት ምስማር በተመሳሳይ ቀረጥ ከውጭ አስመጥቶ መሸጥ የቀለለ እንደሆነ፣ የምስማር አምራቾች ከአስመጭዎች የተሻለ ከለላ እንደሚያስፈልጋቸው በመግለጽ አቤቱታቸውን አቅርበዋል፡፡

ነገር ግን የጥናት ቡድኑ “ይህ ጉዳይ ወደፊት ሊጠና ይገባል” በማለት ጉዳዩን በቀላሉ እንዳለፈውም ይጠቁማሉ፡፡ በምስማር ፋብሪካዎች የተነሱት ሥጋቶችና ችግሮች ከከለላው መነሳት ጋር ተያይዘው ካልተመለሱ የታሪፍ ከለላ ብቻ ማንሳቱ ለአንዱ ወገን ያደላ መሆኑን፣ ይህም የመልካም አስተዳደር እንዲሁም ፍትሐዊነት ጥያቄ የሚያስነሳ ነው በሚል ኩባንያዎቹ የቅሬታቸውን ስፋት በጽሑፍ አቅርበዋል፡፡ የተወሰደው ዕርምጃ ያስገኛል ተብሎ ከሚጠበቀው ፋይዳ አንፃር ሲታይ ያስከተላቸው ችግሮች ሚዛን የደፉ በመሆናቸው፣ ወደ ተግባር ሲለወጥም የተገመቱ ሥጋቶችን ለመከላከል አስቸጋሪ ስለሆነና እንዲሁም በውሳኔው ችግሮች ሲከሰቱ ለመፍታት የሚያስችል ሥርዓት አብሮ ያልታየ በመሆኑ፣ በብዙ መመዘኛዎች ሲታይ በስታፋ ብረት ላይ የተነሳው ከለላ እንደገና ሊጠና ይገባል በማለት ምስማር አምራች ኩባንያዎች ቅሬታቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አቅርበዋል፡፡

ስቲሊ አርኤምአይ በመስከረም 1997 ዓ.ም. በ486 ሚሊዮን ብር ኢንቨስትመንት የብረት ማቅለጥና የሮሊንግ ፋብሪካ በማቋቋም ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ ከዚህ በመቀጠል ኩባንያው አቅሙን በማሳደግ በአገር ውስጥ የሚመረት ስታፋ ብረት ባለመኖሩ በ726 ሚሊዮን ብር ወጪ ታኅሳስ 2006 ዓ.ም. አዲስ ፋብሪካ አቋቁሟል፡፡ ድርጅቱ በአጠቃላይ ሦስት ፋብሪካዎች አሉት፡፡ እነዚህ ፋብሪካዎች በዓመት 30 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል በመጠቀም የአርማታ ብረትና ስታፋ ብረት ያመርታሉ፡፡ ስቲሊ አርኤምአይ ያቋቋመው አስመን ኩባንያ በበኩሉ ስታፋ ብረት በመጠቀም የተለያዩ ምስማሮችን ያመርታል፡፡ ስቲሊ አርኤምአይ ለሪፖርተር በሰጠው መግለጫ፣ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ልማት ፖሊሲና ስትራቴጂ የግል ባለሀብቶች ወደ ኢንዱስትሪ ልማት ቀድመው ለሚገቡ ባለሀብቶች መንግሥት ሰፊና ጠንካራ ድጋፍ እንዳደረገለት አስረድቷል፡፡ “ይህ ከለላ የተሰጠው ለስቲሊ ሳይሆን ለብረት አምራች ኢንዱስትሪ ስለሆነ የኋልዮሽ የእሴት ጭማሪ አድርገው መዋለ ንዋያቸውን ላፈሰሱ ባለሀብቶች የተሰጠ ነው፤” በማለት አቶ ተፈራ ገልጸዋል፡፡ “በዚህ መሠረት ወደ ኢንዱስትሪው ቀድመው ለሚገቡም ሆነ የምርት ሰንሰለቱን ጠብቀው ለሚሠሩ፣ የታክስ ከለላና ሌሎችንም ማበረታቻዎች ይሰጣል፤” በማለትም መንግሥት ያደረገለትን ድጋፍ አስረድቷል፡፡ ኩባንያው በመቀጠል መንግሥት እነዚህን ማበረታቻዎች የሚሰጠው ባለሀብቶች በእነዚህ ማበረታቻዎች ተበረታተው በሰፊው ወደ ልማቱ እንዲገቡና በአገሪቱ የተያዘው የኢንዱስትሪ ስትራቴጂ ግቡን እንዲመታ ለማድረግ እንጂ፣ የተወሰኑ ሰዎችን ጠቅሞ ሌላውን ለመጉዳት አይደለም ብሏል፡፡ 

ኩባንያው የቀረበበትን ክስ በሚመለከት እንደገለጸው፣ ከአሁን በፊት ስታፋ ብረት ከሚጠይቀው የተራቀቀ ቴክኖሎጂ፣ ዕውቀትና ከፍተኛ የካፒታል መጠን ምክንያት በአገሪቱ የማይመረት ነበረ፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ ስቲሊ አርኤምአይ ለአርማታ ብረት እንደተደረገው ሁሉ የስታፋ ብረት በአገር ውስጥ በመመረቱና ምንም እንኳ ስታፍ ብረት ከአርማታ ብረት ጋር ሲነፃፀር የሚጠይቀው የማምረቻ ሒደትና የሚፈጀው ወጪ ከፍተኛ ቢሆንም፣ ለአርማታ ብረት ከተሰጠው የታክስ ከለላ እኩል ከለላ እንዲሰጠው መንግሥት ወስኗል፡፡ ይህም ምስማር ፋብሪካዎች ያቀረቡት በዘርፉ ውስጥ ለአንድ ዓይነት ምርት ብቻ ከለላ ተሰጥቷል የሚለው ትክክል አለመሆኑን ያስረዳል ሲሉ አቶ ተፈራ ተናግረዋል፡፡ 

“ይህ ማለት ከአሁን በፊት ለምስማር ጥሬ ዕቃነት በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከውጭ ሲገባ የነበረው የስታፋ ብረት ላለፉት አሥራ አምስት ዓመታት ሲደረግለት የነበረው የታክስ ከለላ ተነስቶ ቀረጥ እንዲቀረጥበት አደረገ እንጂ፣ ከውጭ ማስመጣት አልተከለከለም፤”  በማለት የስቲሊ አርኤምአይ መረጃ ይተነትናል፡፡

“ይህ የመንግሥት ውሳኔ የስታፋ ምርት በከፍተኛና በብዛት አገር ውስጥ የሚመረት በመሆኑ ካለው የኢንዱስትሪ ፖሊሲና የአገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ቁጠባ ከማጎልበት አንፃር ተመልክቶ የወሰነው ጉዳይ ነው፡፡ ውሳኔውም የተሰጠው ለእኛ ድርጅት ሳይሆን ለምርቱ የተሰጠ ዕውቅና ነው፤” በማለትም አክሏል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአንድ ወገን ስቲሊ አርኤምአይ በሌላ ወገን ደግሞ በርካታ ምስማር አምራቾች በከፍተኛ ደረጃ በመወዛገብ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህንን ውዝግብ ለመፍታት የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴርና የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ያዳረጓቸው ጥረቶች ያልተሳኩ በመሆናቸው፣ ቅሬታ አቅራቢዎቹ መንግሥት በመስከረም 2005 ዓ.ም. ባሳተመው የኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂ ሰነድ ላይ በተዘረዘረው መሠረት ልንስተናገድ ይገባል በማለት ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ጉዳያቸውን መውሰዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

 

ከአዲስ አበባ ወደ ጎጃም ለሌላ ለቅሶ በመሄድ ላይ የነበሩ ዜጎች ተደብድበው ተመልሰዋል በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ሰኔ 8/2007 ዓ.ም ደብረማርቆስ ከተማ የተገደለው የሳሙኤል አወቀ ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ፡፡ አመራሮቹና አባላቱ ዛሬ ሰኔ 13/2007 ዓ.ም በጠዋት ከአዲስ አበባ ተነስተው የሳሙኤል አቀወ ቤተሰቦች ወደሚገኙበት ምስራቅ ጎጃም ዞን ግንደወይን እያቀኑ በነበረበት ወቅት አባይ ድልድይ ላይ […]

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ በደቡብ ክልል አንድ የምርጫ አስተባባሪው አርብለት ተገድለው መገኘታቸውን አስታወቀ። የተቃዋሚ ፓርቲም በምርጫ 2007 ዙሪያ የዛሬውን ጨምሮ 4 አባላቱና ደጋፊዎቹ መገደላቸውን አስታውቋል። በዚህ ሳምንት እንደተገደሉ ተቃዋሚዎች ከገለጿቸው ሶስት ሰዎች በተጨማሪ በኦሮሚያና ደቡብ ክልል ህይወታቸው ማለፉ የተገለጸው አጠቃላይ ቁጥር ስድስት ደርሷል። በደቡብ ክልል ሀዲያ ዞን ሶሮ ወረዳ የተገደሉት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ በትናንትናውለት በሁለት […]