እስራኤላዊው ምሁር ከስደት ተመላሽ ወገኖች አክራሪነት እንዳላጠላባቸው እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል አሉ

እስራኤላዊው ምሁር ከስደት ተመላሽ ወገኖች አክራሪነት እንዳላጠላባቸው እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል አሉ

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥርጣሬውን አጣጥሏል

በዓለም አቀፍ የፀረ ሽብር ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪና በእስራኤል መንግሥት የዲፕሎማሲና የስትራቴጂ ተዛምዶ ማዕከል አማካሪ የሆኑት ዶ/ር ዮናታን ፋይን፣ ኢትዮጵያ ከስደት የምትመልሳቸው ዜጐቿ ከአክራሪነት ጥላ የራቁ መሆናቸውን

ማረጋገጥ እንደሚገባት አሳሰቡ፡፡ የደኅንነትና ዓለም አቀፍ ጥናት ምሁሩ ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት ከየመን፣ ከሊቢያና ከሌሎችም የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ወደ አገር ቤት በሚመለሱ ዜጐች ላይ መንግሥት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡

ዓለም አቀፍ የሽብር ቡድኖችና ጽንፈኛ እምነትን የሚያራምዱ ግለሰቦችና ድርጅቶች በሞሉባቸው የመካከለኛው ምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ አገሮች በብዛት የሚገኙት ኢትዮጵያውያን፣ በአንድም ሆነ በሌላ አጋጣሚ በእነዚህ አካላት ተፅዕኖ ሥር ወድቀው ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡ ይህም እነዚህ ወገኖች ወደ አገራቸው ገብተው ከሚገጥሙዋቸው የመልሶ መዋሀድ ተግዳሮቶች ጋር ተዳምሮ ላልተፈለገ የባህርይ ለውጥ ሊዳርጋቸው እንደሚችል ምሁሩ ገልጸዋል፡፡

ይህ ጥርጣሬ ለምን እንደገባቸው ተጠይቀው የመለሱት ምሁሩ፣ በተለያዩ የዓለም አገሮች የተደረጉ ጥናቶች የሚያሳዩት መረን ላወጣ አፈንጋጭነትና አክራሪነት እርሾ የሚሆኑት ባህርያት በሆነ ወቅት ወደ አገር ቤት ተመልሰው መኖር በሚጀምሩ ዜጎች ምክንያት የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ በተለይ በርካታ ዜጐቿን በስደት የምታጣው አፍሪካ ዜጎቿ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች ከሚገጥማቸው የኑሮ ውጣ ውረድ ጋር ተዳምሮ፣ ለአዳዲስና የኑሮ ሁኔታን ሊቀይሩ ይችላሉ ለተባሉ አስተሳሰቦች በቀላሉ የመንበርከክ ዕድል እንዳላቸውም ገልጸዋል፡፡ በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በምዕራብና በመካከለኛው አፍሪካ የሚገኙ በርካታ ዜጐች በእነዚህ አዳዲስ አስተሳሰቦች በመማረካቸው ምክንያት ወደ አገራቸው ሲመለሱም ይህንኑ አቋማቸውን እንደሚገፉበት ምሁሩ ያስረዳሉ፡፡

እስራኤላዊው ምሁር እስካሁን ድረስ በኢትዮጵያ የሚታየው ሁኔታ በዚህ ደረጃ የሚጠቀስ አለመሆኑን፣ የሕዝቡ የረጅም ዘመናት ተቻችሎ የመኖር ልማድ ለዚህ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን እንደሚያምኑ ገልጸው፣ ነገር ግን ይህ ሁኔታ በተለያዩ የውጭ ተፅዕኖዎችና አካባቢያዊ ሁኔታዎች ሊሸረሸር እንደሚችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ለዚህም ኢትዮጵያ የምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋትና ለአደገኛ ቡድኖች አመቺ ሥፍራ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ 

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ፣ የምሁሩ አስተያየት ምንም መሠረት የለውም ባይባልም ዓለም አቀፋዊ ገጽታን የተላበሰ መሆኑን በመጠቆም፣ ለጊዜው ግን ሥጋትን የሚያጭር አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህንን ጉዳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በቀጥታ ባይመለከተውም፣ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ተገቢውን ሥራ እንደሚያከናውን እገምታለሁ፡፡ በእኛ በኩል ከየትም አገር የሚመጣ ዜጋ በኤምባሲዎችና በቆንስላዎች አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ ሲያሟላ እናስተናግዳለን፤›› ሲሉ አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀዳሚ ዓላማም የዜጐችን ማንነትና ምንነት ማጥናት ሳይሆን፣ የነፍስ አድን ተግባሩን በማቀላጠፉ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ 

እንደ ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አይኦኤም መረጃ፣ በየመን ብቻ ከ50 ሺሕ በላይ ኢትዮጵያውያን መኖራቸው ሲታወቅ እስካሁን ድረስ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸው ታውቋል፡፡ በሊቢያ የሚገኙ ዜጐችም በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆናቸውንም የድርጅቱና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጀመረውን የነፍስ አድን ዘመቻ አጠናክሮ እንደሚቀጥልበት፣ በየትኛውም አገር የሚገኝ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ሊጠቀምበት የሚችል ዕድል መሆኑንም አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በእስራኤል የሚገኙ ቤተ እስራኤላውያንን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ምንም የቀረበ ጥያቄ አለመኖሩን፣ ጥያቄው ከቀረበ ግን እነሱንም ለመርዳት መንግሥት ዝግጁ መሆኑን አቶ ተወልደ አስታውቀዋል፡፡

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን ለሪፖርተር ያጋሩት እስራኤላዊው ምሁር ዶ/ር ዮናታን፣ ኢትዮጵያውያኑ ቤተ እስራኤላውያን በእስራኤል እየገጠማቸው ያለው ፈተና አሳሳቢ መሆኑን፣ በአንዳንድ ምግባረ ብልሹ የፀጥታ ኃይሎች የሚፈጸመውን ጥቃትም አጥብቀው የሚቃወሙ በርካታ እስራኤላውያን መኖራቸውን በመጠቆም፣ የቤተ እስራኤላውያኑ የመብት ጥያቄዎች ሁሉ ምላሽ ሊያገኙ እንደሚገባቸው አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህ የዘር መድልኦ ዛሬም ድረስ በአሜሪካና በሌሎችም ያደጉ አገሮች የሚስተዋል በመሆኑ፣ የእስራኤልን ሁኔታ አዲስ አያደርገውም፡፡ ከዚህ በፊት ሩሲያውያንን ጨምሮ ሌሎችም ትውልደ እስራኤላውያን በተመሳሳይ ችግር ውስጥ አልፈው እዚህ በመድረሳቸው፣ ቤተ እስራኤላውያኑም በቅርብ ጊዜ ችግራቸው እንደሚፈታ እገምታለሁ፤›› በማለት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተደጋጋሚ የሚከሰተውን የቤተ እስራኤላውያን ቁጣና የእስራኤል ባለሥልጣናትን ዘገምተኛ የመፍትሔ ዕርምጃ ገልጸውታል፡፡