የአዲስ አበባ ምክር ቤት ለቀጣዩ በጀት ዓመት 31.8 ቢሊዮን ብር አፀደቀ

ለካፒታል ፕሮጀክቶች 65 በመቶ ተመደበ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ለ2008 ዓ.ም. 31.8 ቢሊዮን ብር በጀት ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. አፀደቀ፡፡ ይህ በጀት ከ2007 ዓ.ም. በጀት ጋር ሲነፃፀር የ14 በመቶ ብልጫ አለው፡፡

ከተያዘው በጀት 65 በመቶ ለካፒታል ፕሮጀክቶች፣ 35 በመቶ ለመደበኛ ወጪዎች ተመድቧል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካፀደቀው በጀት ውስጥ በማዕከል ደረጃ ለሚካሄዱ የካፒታል ፕሮጀክቶች 16.9 ቢሊዮን ብር፣ ለመደበኛ ወጪዎች 5.2 ቢሊዮን ብር፣ ለመጠባበቂያ 1.99 ቢሊዮን ብር መድቧል፡፡ በክፍላተ ከተሞች ለሚካሄዱ የካፒታል ፕሮጀክቶች 2.2 ቢሊዮን ብር፣ ለመደበኛ ወጪዎች 5.5 ቢሊዮን ብር ተመድቧል፡፡ 

ይህ ትልቅ በጀት የሚሸፈነው ከተለያዩ የገቢ ምንጮች ነው፡፡ ከአገር ውስጥ ታክስ ገቢ 22.97 ቢሊዮን ብር፣ ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች 2.9 ቢሊዮን ብር፣ ከማዘጋጃ ቤታዊ ገቢዎች 2.98 ቢሊዮን ብር፣ ከመንገድ ፈንድ 50.4 ሚሊዮን ብር ለማግኘት መታቀዱን የበጀቱ ረቂቅ ያመለክታል፡፡ በፌዴራል መንግሥት አማካይነት ከውጭ አገሮች በተለይ በብድር መልክ 2.6 ቢሊዮን ብር፣ ከዕርዳታ ደግሞ 238 ሚሊዮን ብር ይገኛል ተብሎ ታቅዷል፡፡ በወጪ ደረጃም 12.7 ቢሊዮን ብር ለመደበኛ የተመደበ ሲሆን፣ 19.09 ቢሊዮን ብር ለካፒታል ወጪ ተበጅቷል፡፡ ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የቀረበው በጀት አዋጅ እንደሚያስረዳው፣ ከተያዘው በጀት ትልቁ ተጠቃሚ የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣንና የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ናቸው፡፡ 

መንገዶች ባለሥልጣን 156.9 ሚሊዮን ብር ለመደበኛ የተያዘለት ሲሆን፣ 5.9 ቢሊዮን ብር ደግሞ ለካፒታል ፕሮጀክቶች ተመድቦለታል፡፡ ለውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን 1.2 ቢሊዮን ብር ለመደበኛ በጀት ሲያዝለት፣ 4.4 ቢሊዮን ብር ደግሞ ለካፒታል ፕሮጀክቶች ተመድቦለታል፡፡ 

የከተማው ምክር ቤት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት (2007 ዓ.ም.) 27.9 ቢሊዮን ብር ማፅደቁ ይታወሳል፡፡ በተጠናቀቀው በዚህ በጀት ዓመት በማዕከል ደረጃ ለሚገነቡ የካፒታል ፕሮጀክቶች 16.6 ቢሊዮን ብር፣ ለመደበኛ ወጪዎች 4.1 ቢሊዮን ብር፣ ለመጠባበቂያ ደግሞ 1.4 ቢሊዮን ብር መመደቡ ይታወሳል፡፡ በክፍላተ ከተሞች ለሚካሄዱ የካፒታል ፕሮጀክቶች 1.6 ቢሊዮን ብር፣ ለመደበኛ ወጪዎች 4 ቢሊዮን ብር መመደቡ አይዘነጋም፡፡ 

ከንቲባ ድሪባ ኩማ ባቀረቡት የ2007 ዓ.ም. ዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ባለፉት 11 ወራት 25.674 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ የተሰበሰበው 19.4 ቢሊዮን ብር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህም የዕቅዱን 75 በመቶ ብቻ ያሳካ ነው፡፡ 

ከዚህ በጀትም ለመደበኛና ለካፒታል ወጪዎች 15.6 ቢሊዮን ብር የተከፈለ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ አምስት ቢሊዮን ብር (32.11 በመቶ) ለመደበኛ፣ 10.6 ቢሊዮን ብር (68 በመቶ) ለካፒታል ወጪዎች ማስፈጸሚያ መሆኑ ተመልክቷል፡፡ 

‹‹በአጠቃላይ የገቢ አፈጻጸማችን ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር ዕድገት ያሳየ ቢሆንም፣ ከዕቅዳችን አኳያ ሲታይ ዝቅተኛ ነው፡፡ በቀጣይነት የገቢ መሠረቱን የማስፋት፣ የሕግ ማስከበር ሥራዎችን የማጠናከርና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ መሰብሰብ የሁሉንም አካላት ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ነው፤›› በማለት የከንቲባ ድሪባ ሪፖርት በቀጣዩ ዓመት የተሻለ አፈጻጸም ማሳየት አስፈላጊነት ላይ አፅንኦት ሰጥቷል፡፡ 

 

በሁለቱ የጡረታ አዋጆች ላይ የተካተተው ማሻሻያ ከፕሬዚዳንቱ ሥልጣን ጋር ይጋጫል የሚል ክርክር አስነሳ

በግል ድርጅት ሠራተኞች የጡረታ አዋጅና በመንግሥት ሠራተኞች የጡረታ አዋጅ ላይ የተደረጉ ማሻሻያዎችን እንዲያፀድቅ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀረበለት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማሻሻያዎቹን ቢቀበላቸውም፣ ተፈጻሚ

የሚሆኑበት ጊዜ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ከመፈረማቸውና በነጋሪት ጋዜጣ ከመታወጃቸው በፊት ሊሆን አይገባም የሚል ክርክር ተነሳ፡፡

ምክር ቤቱ ሰኔ 29 ቀን ባደረገው ጉባዔ ካፀደቋቸው ረቂቅ አዋጆች መካከል፣ የመንግሥት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅና የግል ድርጅት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ላይ የተደረጉት ማሻሻያዎች ይገኙበታል፡፡ ከሁለቱ አዋጆች መካከል የግል ድርጅቶች ጡረታ አዋጅ ማሻሻያ ቀደም ሲል አማራጭ አድርጎ ያቀረበውን የፕሮቪደንት ፈንድ ሥርዓት የሚያነሳ አንቀጽ በማካተቱ፣ በርካታ ድርጅቶች ተቃውሟቸውን ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ ከዚህም ውጪ ይህ አዋጅ በመንግሥት ድርጅቶች የተጠራቀሙ በፕሮቪደንት ፈንድ የሚተዳደር ገንዘብ ወደ ግል ጡረታ እንዲዘዋወር የሚል አንቀጽ በማስገባቱ፣ ከፍተኛ ሥጋትን በግል ሠራተኞች ላይ ፈጥሮ ነበር፡፡ 

ይህንን ሥጋት የቀረፈ ማሻሻያ ፓርላማው አንቀጹን በመሠረዝ ያደረገ ቢሆንም፣ በፕሮቪደንት ፈንድ የታቀፉ ድርጅቶች አሁንም በምርጫው ይቀጥሉ የሚለውን ጥያቄ ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ ሁለቱ አዋጆች ላይ ማሻሻያ ያቀረቡት የመንግሥት ድርጅቶች ጡረታ ኤጀንሲና የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ጡረታ ኤጀንሲ አዋጆቹ የሚፀኑበትን ጊዜ በነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ከወጡ በኋላ በሚል አስቀምጠው የነበረ ቢሆንም፣ የፓርላማው የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሁለቱም አዋጆች ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ የፀኑ ይሆናል በሚል አሻሽለውታል፡፡ 

ጉዳዩን በተመለከተ አንድ የፓርላማ አባል፣ ‹‹አዋጆች ተፈጻሚ መሆን የሚጀምሩት በሕገ መንግሥቱ መሠረት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፈርመውበት በነጋሪት ጋዜጣ ታውጆ ነው፡፡ ይህ ማሻሻያ አዋጅ የተለየ አሠራር ያመጣው ለምንድነው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ማሻሻያ አዋጁ እንዲፀድቅ ለፓርላማው የውሳኔ ሐሳብ ያቀረቡት የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አበባ ዮሴፍ፣ ከበጀት ዓመቱ ጋር የተጣጣመ ለማድረግ እንዲሆን ጠቁመው፣ የበለጠ ግን በምክር ቤቱ የሚገኙ የሕግ ባለሙያዎች አስተያየት እንዲሰጡበት ጠይቀዋል፡፡ 

በዚሁ መሠረት የሕግ ባለሙያዎች አስተያየት እንዲሰጡ አፈ ጉባዔው በጋበዙት መሠረት፣ የምክር ቤቱ የመከላከያና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ዳባ የተነሳውን የሕገ መንግሥት ጥያቄ በመደገፍ መስተካከል እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ‹‹ሕገ መንግሥት የመሸርሸር ጉዳይ እንዳይሆን ፍርኃት አለኝ፡፡ በሕገ መንግሥቱ ለፕሬዚዳንቱ ከተሰጡ ሥልጣኖች ውስጥ አንዱ ይኼ ነው፤›› በማለት ሐሳባቸውን ገልጸዋል፡፡ 

በማከልም ሕግ ሲወጣ በተቻለ መጠን ምንም ዓይነት ውዥንብር መፍጠር እንደሌለበት የተናገሩት አቶ ተስፋዬ፣ ‹‹አዋጁ ተፈጻሚ መሆን ያለበት በፕሬዚዳንቱ ተፈርሞ በነጋሪት ጋዜጣ ከወጣ በኋላ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ ተፈጻሚ ቢሆን ዓላማው ገንዘብ የመሰብሰብ ያስመስለዋል፡፡ ስለዚህ አሠራራችንን ባንጥስ የሚል አስተያየት አለኝ፤›› ብለዋል፡፡ ሌላኛው የሕግ ባለሙያ የፓርላማው፣ የሕግ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አስመላሽ ወልደ ሥላሴ፣ ‹‹የሕግ ክርክር ለማንሳት አይደለም፡፡ በዚህ ምክር ቤት ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት አዋጆች የሚፀኑበትን ቀን ማስቀመጥ ይቻላል፡፡ ሳያስቀምጥም ዝም ሊል ይችላል፡፡ ከአንድ ዓመት በኋላ ተፈጻሚ ሊሆን ይችላል ብሎ ሊወስንም ይችላል፤›› በማለት ተቃርነዋል፡፡ 

ሕገ መንግሥቱ የሚለው ፕሬዚዳንቱ በ15 ቀናት ውስጥ ይፈርማሉ እንጂ፣ ከአሥራ አምስተኛው ቀን በኋላ እንደማይል የተናገሩት አቶ አስመላሽ፣ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ የፀና ይሆናል መባሉ ፕሬዚዳንቱን ከመፈረም እንደማያግዳቸው ተናግረዋል፡፡ ‹‹ጉዳዩ የፕሮሲጀር ጉዳይ ስለሆነ ምክር ቤቱ በቀረበው መልኩ ቢቀበለው ችግር የለውም፡፡ ከሕገ መንግሥቱም ሆነ ከሌሎች ሕጎች ጋር አይጋጭም፤›› ብለዋል፡፡ በዚሁ የአቶ አስመላሽ ማብራሪያ መሠረት የመንግሥት ጡረታ አዋጅ ላይ የተደነገገው ማሻሻያ ላይ ተቃውሞ አቅርበው የነበሩትን አቶ ተስፋዬ ዳባን ጨምሮ፣ በሰጡት ድምፅ ያለ ተቃውሞ በሙሉ ድምፅ ፀድቋል፡፡ 

ቀጥሎ የቀረበው የግል ድርጅቶች ማሻሻያ የውሳኔ ሐሳብም በተመሳሳይ አዋጁ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ እንዲፀና የሚጠይቅ ነው፡፡ ይህ የውሳኔ ሐሳብ በቀረበበት ወቅት በድጋሚ ዕድል ያገኙት አቶ ተስፋዬ ዳባ፣ ‹‹አቶ አስመላሽ ያነሱትን መከራከሪያ አከብራለሁ፤›› ብለዋል፡፡ አክለውም እርሳቸው የተለከቱት ከመብት አንፃር መሆኑን፣ አቶ አስመላሽ ደግሞ ከሥነ ሥርዓት (Procedure) አንፃር መሆኑን በዚህም መሠረት፣ ‹‹ሁለታችንም ኤ ነው ያገኘነው›› በማለት ምክር ቤቱን ፈገግ አሰኝተዋል፡፡ 

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የሕግ ባለሙያዎች ግን አዋጆች ተፈጻሚ መሆን ያለባቸው በነጋሪት ጋዜጣ ከታተሙ በኋላ መሆን እንዳለበት ይከራከራሉ፡፡ ፓርላማው ራሱ ያወጣው የፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ማቋቋሚያ አዋጅ 3/1995 አንቀጽ 2(2) ማናቸውም የፌዴራል መንግሥት ሕግ የሚወጣው በፌዴራሉ ነጋሪት ጋዜጣ ይሆናል እንደሚል፣ በነጋሪት ጋዜጣ የወጣን ሕግ ማንኛውም ኅብረተሰብ የማወቅና የመቀበል ኃላፊነት እንዳለበት ይገልጻሉ፡፡ 

በዚሁ ማቋቋሚያ አዋጅ አንቀጽ 2(3) ላይ፣ ‹‹ማናቸውም የፌዴራል ወይም የክልል ሕግ አውጪ፣ አስፈጻሚና ተርጓሚ እንዲሁም ማንኛውም የተፈጥሮ ሰው ወይም በሕግ የሰውነት መብት የተሰጠው አካል በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ የሚወጣ ሕግን የመቀበል ግዴታ ይኖርበታል፤›› እንደሚል የሚጠቅሱት የሕግ ባለሙያዎች፣ ፓርላማው ያፀደቀውን ሕግ ኅብረተሰቡ አውቆታል ተብሎ የሚገመተው በነጋሪት ጋዜጣ ከወጣ በኋላ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ 

በመሆኑም በነጋሪት ጋዜጣ ያልወጣን ሕግ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ ተፈጻሚ ይሆናል ብሎ አንቀጽ ማስገባት፣ አዋጁ ተፈጻሚ በሚሆንባቸው ዜጎች ወይም ድርጅቶች ላይ ጉዳት ሊያመጣ ይችላል ሲሉ ይከራከራሉ፡፡ 

በተለይ የፀደቁት አዋጆች ጡረታ ሰብስበው በማያስገቡ ቀጣሪዎች ላይ ወለድና ቅጣት የሚጥሉ በመሆናቸው፣ አዋጁ ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ መፅደቁን የማያውቁ ድርጅቶች ወይም ቀጣሪዎች ላይ የሕግ ተጠያቂነትን መጣል አግባብ አይሆንም ብለዋል፡፡ አቶ ተስፋዬ ዳባ በፓርላማው ስላነሱት ክርክር ተጨማሪ አስተያየት ይኖራቸው እንደሆነ ለማጣራት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡

የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 57 ፕሬዚዳንቱ በአሥራ አምስት ቀናት ውስጥ ባይፈርም፣ ሕጉን በሥራ ላይ ከማዋል የሚያግድ እንደማይሆን ይደነግጋል፡፡ 

 

የግል ባንኮች ትርፍ ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን ይጠበቃል

ንግድ ባንክ ከታክስ በፊት 12 ቢሊዮን ብር ማትረፉ ተሰምቷል

በኢትዮጵያ የባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ 16 የግል ባንኮች በ2007 በጀት ዓመት ከታክስ በፊት ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ እንደሚያገኙ ሲጠበቅ፣ አንዳንድ ባንኮችም የትርፍ ምጣኔያቸውን ከእጥፍ በላይ ማሳደጋቸው ታወቀ፡፡ 

የ2007 ዓ.ም. የባንኮቹ የመጀመሪያ ደረጃ ጥቅል መረጃ እንደሚያሳየው ሁሉም ባንኮች በአትራፊነታቸው ዘልቀዋል፡፡ ከአምናው የበለጠ ትርፍ ማግኘትም ችለዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ሁሉም ባንኮች ከታክስ በፊት አትርፈውት የነበረው ግርድፍ ትርፍ ከ4.6 ቢሊዮን ብር በላይ መሆኑ ይታወሳል፡፡

ሁሉም የግል ባንኮች በ2007 በበጀት የሒሳብ ሪፖርት ተቀናናሽ ሒሳብ ቢኖርባቸውም፣ ጥቅል ትርፋቸው ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ይሆናል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከፍተኛ ትርፍ በማግኘት ዘንድሮም ከግል ባንኮች ከፍተኛውን ትርፍ ያስመዘገበው ዳሸን ባንክ ሲሆን፣ ከታክስ በፊት ከ950 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉ ተጠቁሟል፡፡ በ2006 ዓ.ም. ባንኩ ከታክስ በፊት 928 ሚሊዮን ብር ማትረፉ አይዘነጋም፡፡

አዋሽ ባንክም ወደ 890 ሚሊዮን ብር ገደማ ማትረፉ እየተነገረ ነው፡፡ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከግል ባንኮች በትርፍ መጠኑ ወደ ሦስተኛ ደረጃ ላይ የመጣው የኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በማትረፍ ደረጃውን ይዞ መቀጠሉ ታውቋል፡፡

በበጀት ዓመቱ በትርፍ ምጣኔው ከፍተኛ ዕድገት ካሳዩ ባንኮች መካከል እናት ባንክ አንዱ ሲሆን፣ በበጀት ዓመቱ ከ72 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፍ ችሏል፡፡ ይህ ትርፍ ባለፈው በጀት ዓመት ካገኘው ትርፍ ጋር በንፅፅር ሲቀመጥ ከእጥፍ በላይ ማደጉን ያሳያል፡፡ ባንኩ በ2006 በጀት ዓመት አስመዝግቦት የነበረው ትርፍ 31 ሚሊዮን ብር እንደነበር ይታወሳል፡፡

እንደ እናት ባንክ ሁሉ ከአምናው የትርፍ ምጣኔ ጋር ሲነፃፀር ከ50 በመቶ በላይ ብልጫ ያለው ትርፍ ያስመዘገበው አንበሳ ባንክ ነው፡፡ እንደ ምንጮች ገለጻ የአንበሳ ባንክ በ2007 ዓ.ም. ያልተጣራ ትርፍ 275 ሚሊዮን ብር ደርሷል፡፡ ይህ ትርፍ አምና አስመዝግቦት ከነበረው 127 ሚሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር ከ145 ሚሊዮን ብር በላይ ጭማሪ አሳይቷል፡፡ 

አንበሳ ባንክ በትርፍ ዕድገቱ ብቻ ሳይሆን 580 ሚሊዮን ብር የነበረውን የተቀማጭ ገንዘብ አቅሙን ወደ 1.7 ቢሊዮን ብር በማድረስ ከፍተኛ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉ ይጠቀሳል፡፡

ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ በ2006 ዓ.ም. 131 ሚሊዮን ብር የነበረውን ትርፍ ወደ 140 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ ንብ ባንክ ከ430 ሚሊዮን ብር በላይ እንዳተረፈ ሲነገር፣ አምና 350 ሚሊዮን ብር ያተረፈው አቢሲኒያ ባንክ ደግሞ ከ365 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉ ተጠቁሟል፡፡ ደቡብ ግሎባል ባንክም ከአምናው በተሻለ ከታክስ በፊት 31 ሚሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል፡፡ ይህ ትርፍ ከሁሉም ባንኮች ያነሰ ነው፡፡ ባንኩ አምና ያገኘው ትርፍ 19 ሚሊዮን ብር ነበር፡፡

ሌሎቹም ባንኮች የትርፍ ምጣኔያቸው ዕድገት የተለያየ ቢሆንም፣ የትርፍ ዕድገት በማሳየታቸው በአጠቃላይ የግል ባንኮችን የትርፍ መጠን አምና ከነበረበት ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ያሳድገዋል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ 

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2007 በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ከታክስ በፊት ማትረፉ ተሰምቷል፡፡ ንግድ ባንክ ባለፈው ዓመት 9.7 ቢሊዮን ብር ከታክስ በፊት ማትረፉ ይታወሳል፡፡ የዘንድሮው ግን ትልቅ ትርፍ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ 

 

ሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የምርጫው ውጤት ሰላማዊውን ትግል ውስብስብ አድርጎታል አሉ

በአምስተኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ የተሳተፉት የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) እና የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ) የምርጫው ውጤት ሕዝቡን ወዳልተፈለገ

አቅጣጫ ሊያመራ ይችላል የሚል ሥጋት እንዳላቸው አስታወቁ፡፡ ሰላማዊውን የፖለቲካ ትግል ውስብስብ እንዳደረገውም ገልጸዋል፡፡

ፓርቲዎቹ ይህንን ያስታወቁት ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. በራስ ሆቴል በጋራ በሰጡት መግለጫ ወቅት ሲሆን፣ መግለጫውን የሰጡት ደግሞ የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሐሪ፣ የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደና የኢራፓ ፕሬዚዳንት አቶ ተሻለ ሰብሮ ናቸው፡፡

ሥርዓቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ ፍሬያማ ከመሆን ይልቅ እየቀጨጨና እየኮሰመነ በመሄድ ላይ ለመሆኑ ለመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ዋና መገለጫ የሆነው የምርጫ ሒደት ችግር ቁልጭ አድርጐ እያሳየን ሲሉም ደምድመዋል፡፡ 

የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት እውን እንዳይሆን ገዥው ፓርቲ እንቅፋት ሆኗል የሚለው የፓርቲዎቹ መግለጫ፣ ‹‹ገዥው ፓርቲ ከዚህ ግትር አቋሙ ፈቀቅ የማይል ከሆነ የአገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታም ሆነ አጠቃላይ የአገሪቱ ሰላም አጣብቂኝ ውስጥ ይገባል ብለን እናምናለን፡፡ ገዥው ፓርቲ የምርጫ ዴሞክራሲያዊነትና ፍትሐዊነት መርሆዎችን ካላከበረ ሕዝቡን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ይመራዋል ብለን እንሰጋለን፤›› ሲልም ያክላል፡፡ የምርጫውን ውጤት ተከትሎ የከሰመው የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት በአገሪቱ ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ጥያቄ ያስቀመጠ መሆኑንም ፓርቲዎቹ አመልክተዋል፡፡  

‹‹በ2007 ዓ.ም. የተከናወነው አምስተኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ባለመሆኑ ምክንያት፣ በአገራችን የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ላይ ጥቁር ነጥብ ጥሏል፡፡ ይህም በመሆኑ በአገራችን ያለው አንፃራዊ ሰላም አስተማማኝ አይሆንም የሚል ሥጋት አድሮብናል፤›› በማለትም የፓርቲዎቹ ፕሬዚዳንቶች በጋራ በሰጡት መግለጫ አስረድተዋል፡፡ 

‹‹በአገራችን ዴሞክራሲ እንዲጠናከርና እንዲያብብ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ተብለው የሚጠበቁ ተቋማት በምርጫው ሒደት ላይ የፈጠሯቸው ተግዳሮቶች በሰላማዊ ትግሉ ላይ ትልቅ ጋሬጣ በመሆናቸው፣ የወደፊቱን ሰላማዊ ትግል እጅግ ውስብስብና አስቸጋሪ አድርጐታል፤›› በማለት በመግለጫው አትቷል፡፡

የፓርቲዎቹን አጠቃላይ የወደፊት አቅጣጫ በተመለከተ የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሐሪ ሲናገሩ፣ ‹‹ከሦስቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሁለቱ የጋራ ምክር ቤት አባል ናቸው፡፡ እኛ ግን አይደለንም፡፡ ልንሆንም አንችልም፡፡ ሙሉ በሙሉ በአጠቃላይ ጉዳዮች ላይ አብረን እንሠራለን ማለት አይደለም፤›› በማለት ለጊዜው በጋራ የሚሠሩት በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡

በጋራ ለመሥራት ከተስማሙባቸው ጉዳዮች መካከል ጋዜጣዊ መግለጫዎችን በጋራ መጥራትና የተቃውሞ ሰላማዊ ሠልፎችን ማዘጋጀት ይጠቀሳሉ፡፡ ‹‹ሙሉ በሙሉ በአንድ ላይ ለመሄድ የምናርቃቸውና የምንመለከታቸው ጉዳዮች ይኖራሉ፤›› በማለትም ፓርቲዎቹ በጋራ የሚሠሩባቸውን ተጨማሪ ጉዳዮች ለመለየት በድርድር ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡ 

የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፣ ‹‹በተለይ ተመሳሳይ ርዕዮተ ዓለም የምናራምድ ፓርቲዎች በተጠናከረ ስልትና ስትራቴጂ ሐሳቦቻችንን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ግልጽ እያደረግን ለመሥራት እንድንችል የሚያስችለንን ስልት ነድፈን እንሄዳለን ብለን እናምናለን፤›› በማለት ሦስቱ ፓርቲዎች የሚያግባቧቸውን ጉዳዮች ሙሉ በሙሉ እንዳለዩ ገልጸዋል፡፡

ኅብረት፣ ግንባር ወይም ውህደት ፈጥሮ ለመሥራት በርካታ ሒደቶችን የሚጠይቅ በመሆኑ ይህንን በሌሎች የፖለቲካ ተንታኞችም እየታገዝን በጉዳዩ ላይ ወደፊት እንወስናለን፤›› በማለት ሐሳባቸውን አጠቃለዋል፡፡

በምርጫ 97 ጠንካራ ተወዳዳሪ የነበረው ቅንጅት እንዲዳከም ትልቅ በር የከፈተው የመኢአድና የኢዴፓ ጤናማ ያልሆነ ግንኙነት እንደነበር ይታወሳል፡፡ ከቅንጅት ራሱን ያገለለው ኢዴፓ ከምርጫ 97 በኋላ ከተለያዩ ኅብረቶች፣ መድረኮችና ጥምረቶች ራሱን በማግለል የቅንጅት አባል ከነበሩ ፓርቲዎች ጋር አንድ ላይ ለመሥራት የሚያስችል መሠረት እንደሌለ፣ በጫና አባል መሆኑ ስህተት እንደነበር በራሱ ላይ ግለ ሒስ ማቅረቡም የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡

የፖለቲካ ተንታኞች ከዚህ አንፃር ኢዴፓ መሥራች አባላቱ ተገንጥለው የወጡበት መአሕድ ራሱን በሒደት ወደ መኢአድ ከመቀየሩ አንፃርና ኢራፓ ከ1997 በኋላ በ2001 ዓ.ም. የተፈጠረ አዲስ ፓርቲ ከመሆኑ አኳያ፣ ከእነዚህ ፓርቲዎች ጋር የጀመረው ግንኙነት ያልተጠበቀ መሆኑን እየገለጹ ነው፡፡  

 

ውሳኔውን አንብቦ ለመጨረስ ሦስት ቀናት ፈጅቷል

ራሳቸውን የሙስሊሙ ኅብረተሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ በማለት ሃይማኖታዊና ፖለቲካዊ ዓላማዎችን ለማራመድ፣ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመጣል፣ ኢስላማዊ መንግሥት ለመመሥረት፣ በህቡዕ

በመደራጀትና የሽብር ድርጊት ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል ተብለው የሽብርተኝነት ወንጀል ክስ የተመሠረተባቸው 18 ግለሰቦች ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተባሉ፡፡

የፌዴራል ከፍተኛ ዓቃቤ ሕግ ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም. የሽብር ድርጊት ክስ የመሠረተባቸው ሁለት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና 29 ግለሰቦችን የነበረ ቢሆንም፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት ጥፋተኛ ያላቸው 18 ተከሳሾችን ብቻ ነው፡፡ የቀድሞ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ጁነዲን ሳዶ ባለቤት ወ/ሮ ሐቢባ መሐመድ መሐሙድን ጨምሮ 11 ግለሰቦችና ድርጅቶቹ ከክሱ በነፃ መሰናበታቸው ይታወሳል፡፡

ፍርድ ቤቱ ለሦስት ዓመታት ያህል ሲያከራክርና ሲመረምር የከረመውን የፍርድ ሒደት አጠናቆ የጥፋተኝነት ውሳኔ የሰጠው በአቶ አቡበከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ፣ ካሚል ሸምሱ፣ በድሩ ሁሴን፣ ሼክ መከተ ሙሔ፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሐመድ አባተ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ሙራድ ሽኩር፣ አቡበከር ዓለሙ፣ ኑሩ ቱርኪ፣ ሼክ ባህሩ ዑመር፣ ሙኒር ሁሴን፣ ሼክ ሰዒድ ዓሊ፣ ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው፣ ሙባረክ አደምና ካሊድ ኢብራሂም ላይ ነው፡፡

ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በሁሉም ተከሳሾች ላይ አራት ክሶችን ያቀረበ ቢሆንም፣ ሦስተኛና አራተኛ ክሶች የሚያተኩሩት መንግሥታዊ ባልሆኑት ድርጅቶች ላይ በመሆናቸው ድርጅቶቹ ነፃ በመሆናቸው ክሶቹም ቀሪ ሆነዋል፡፡ በአንደኛና በሁለተኛ ክሶች ላይ ተከሳሾቹ ድርጊቱን ክደው በመከራከራቸው ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ ያስረዱኛል ያላቸውን የሰዎችና የሰነድ ማስረጃዎችን አቅርቧል፡፡ ከመቶ በላይ ምስክሮችንም አሰምቷል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ያቀረባቸውን የሰዎችና የሰነዶች ማስረጃዎች ጨምሮ፣ የተከሳሾች መስቀለኛ ጥያቄ የዓቃቤ ሕግን ክስና የምስክሮች ቃል ማፍረስ አለማፍረሱን መርምሮ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾቹም ከ400 በላይ መከላከያ ምስክሮችን አስመዝግበው 157ቱን በማሰማት ቀሪዎቹን ትተዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግና ተከሳሾቹ በምስክሮቻቸው ያስረዱትን የምስክርነት ቃል ከክሱና ተገቢ ሕግ ጋር በመመርመር፣ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. የጥፋተኝነት ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሰብሳቢ ዳኛ በሆኑበት ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት፣ አምስት ጭብጦችን ይዞ የክስ መዝገቡን መመርመሩን ገልጿል፡፡ ፍርድ ቤቱ የያዛቸው ጭብጦች፣ ‹‹መንግሥት በሙስሊሙ ጉዳይ ጣልቃ ገብቷል ወይስ አልገባም? መንግሥት የሙስሊሙን ማኅበረሰብ ከፋፍሏል  ወይስ አልከፋፈለም? የመጅሊሱ ምርጫ በቀበሌ እንዲሆን መደረጉ አግባብ ነው ወይስ አይደለም? ተከሳሾችን ለመያዝ የተደረገው የብርበራ ሒደት የኢትዮጵያን ሕግና ሕገ መንግሥት እንዲሁም ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ስምምነቶችን የተከተለ ነው ወይስ አይደለም? እና ተከሳሾች የቀረበባቸውን ክስ ተከላክለዋል ወይስ አልተከላከሉም?›› የሚሉ ናቸው፡፡

ፍርድ ቤቱ የሰጠው የጥፋተኝነት ውሳኔ ከመቶ ገጾች በላይ በመሆኑ ማንበብ የተጀመረው ሰኔ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ቢሆንም የተጠናቀቀው ከሦስት ቀናት በኋላ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ነው፡፡ ሰኔ 26 ቀን 2007 (ዕለተ ዓርብ) ችሎት አልነበረም፡፡ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ያቀረቡት በርካታ ገጾች ያሉት የሰነድ መከላከያ መስረጃ ማቅረባቸውን ገልጾ፣ ከክሱ ጋር የሚዛመዱትንና ፍሬ ነገር ያለባቸውን ሰነዶች መውሰዱን ገልጾ ባጭሩ አሰማ፡፡

ተከሳሾቹ ከመቀመጫቸው ተነስተው ‹‹ጥያቄ አለን›› በማለት ሲያመለክቱ፣ ‹‹ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እየተነበበ ጥያቄ ማቅረብ አይቻልም፤›› ቢልም መናገራቸውን ቀጠሉ፡፡ እስካሁን መታፈናቸውን (የጥፋተኝነት ውሳኔው እስከተሰጠበት ቀን) ተናግረው ያቀረቡት 20,000 ገጽ ማስረጃ ሆኖ ሳለ አራት ገጽ እንኳን የማይሞላ ማስረጃ ተደርጎ መወሰዱን እንደሚቃወሙ ገለጹ፡፡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን እንዳልሠራው በመናገር ይኽንን ሊያስብላቸው የቻለው በውሳኔው ውስጥ የተፈቱ ሰዎች ስም ዝርዝር ሲጠቀስ በመስማታቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ሠርቶት ቢሆን ኖሮ የተፈቱ ሰዎች ሊካተቱ እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በተነበበላቸው ውሳኔ ውስጥ በርካታ ስህተቶች እንዳሉም አክለዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ በመግባት በተለይ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትሩ ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያምና ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሙስሊሙን ኅብረተሰብ በመሰብሰብ እየከፋፍሉትና የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በመንዛትና ሙስሊሙን ሊከፋፈሉ እንደሆነ በመግለጽ የሃይማኖት ተከታዮችን ማነሳሳታቸውን የዓቃቤ ሕግ ማስረጃዎች እንደሚያረጋግጡ ገልጿል፡፡ የወሃቢያ አስተምህሮ መጥቶ ሃይማኖታቸውን ሊያስቀይራቸው መሆኑን የፌዴራል ጉዳዮች ለሙስሊሞች መንገሩን፣ የአወሊያ ተማሪዎች በመጅሊሱ መባረራቸውን፣ የወሃቢያ አስተምህሮ ሕገ መንግሥቱን ለማፈራረስ የሚንቀሳቀስ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ መናገራቸውን፣ ሙስሊሞች በጨለማ ውስጥ መታሰራቸውን፣ መንግሥት ከአወሊያ ላይ እጁን ያላነሳና መጅሊሱ ያወጣው መተዳደሪያ ደንብ ሙስሊሙን የሚያከብር እንዳልሆነ በመናገር መንግሥት አስቸኳይ መልስ ካልሰጠ፣ በሌላው ዓለም የሚታየው አክራሪነት በኢትዮጵያም የማይታይበት ምንም ምክንያት እንደሌለ፣ ምርጫ ከመስጊድ ውጪ መደረግ እንደሌለበት በመንገርና በመቀስቀስ አመፅ ማነሳሳታቸውን ዓቃቤ ሕግ ካቀረበው የሰነድና የሰው ምስክሮች መረጋገጡን ፍርድ ቤቱ አብራርቷል፡፡

ተከሳሾቹ በተለያዩ ቦታዎች ባደረጉዋቸው ንግግሮች የፖለቲካ አጀንዳ እንደሌላቸው፣ ኢስላማዊ መንግሥት የመመሥረት ዓላማ እንደሌላቸውና ሞኝ አለመሆናቸውን፣ የሚፈልጉት ጥያቄያቸው እንዲመለስላቸው ማለትም የመጅሊስ ምርጫ በመስጊድ እንዲሆንና ታዛቢ እንደማያስፈልግ፣ ሕዝበ ሙስሊሙን የሚወክለው መፍትሔ አፈላላጊው ኮሚቴ ብቻ ምርጫውን የማድረግ ኃላፊነት እንዲወስድ፣ ወዘተ እንዳሉ የገለጹ ቢሆንም፣ ሃይማኖቱን ሽፋን በማድረግ ሙስሊም ኅብረተሰቡን ለአመፅ ማነሳሳታቸውን ዓቃቤ ሕግ በሰነድና በምስክሮች ማረጋገጡን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡

ተከሳሾቹ ሰላማዊ መሆናቸውን፣ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጠላቸውን የሃይማኖት እኩልነትና መንግሥት በሃይማኖት፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጣልቃ አይገቡም የሚለውን ለማረጋገጥ ስለእምነታቸው ከመጠየቃቸው ባለፈ፣ ምንም ወንጀል አለመፈጸማቸውን የሚያስረዱላቸው የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች ማቅረባቸውን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ 

ሁሉም ተከሳሾች ከአንደኛ ተከሳሽ አቶ አቡበከር በስተቀር ዓቃቤ ሕግ ፈጽመዋል ያለውን የወንጀል ድርጊት ፖሊስ በወንጀል ሕግ 27 መሠረት በግዳጅ ቃላቸውን እንዲሰጡ ያደረጋቸው መሆኑን መናገራቸውን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ ነገር ግን ዓቃቤ ሕግ በምስክሮቹና በሰነድ ማስረጃዎቹ ተከሳሾቹ በፖሊስ ጣቢያ አምነው የተናገሩትን በማረጋገጡ፣ ተከሳሾቹ ያቀረቡት የመከላከያ ማስረጃ የዓቃቤ ሕግን ክስ ከማረጋገጥ ባለፈ ከተጠያቂነት የሚያድናቸው አለመሆኑን ገልጿል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የተመሠረተባቸውን ክስ ማስተባበል አለመቻላቸውን አንድ በአንድ ሲገልጽ፣ መጀመርያ አቶ አቡበከር ከመቀመጫቸው በመነሳት ‹‹አሏህ አክበር፣ ነፃነቴን ያረጋገጥኩበት ፍርድ በመሆኑ ደስተኛ ነኝ፤›› ሲሉ፣ ሁሉም እጅ ለእጅ ታይዘው ‹‹አሏህ አክበር›› በማለታቸው ፍርድ ቤቱ ፖሊስ አስፈላጊውን ዕርምጃ እንዲወስድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾቹ መደብዳባቸውንና ከፍተኛ በደል እንደደረሰባቸው በመከላከያ ምስክሮች ቢያስረዱም፣ በተለይ እርስ በርስ (እስረኞቹ) ከመመሰካከራቸው አንፃር ምስክርነቱ ተዓማኒ ሊባል እንደማይችል ፍርድ ቤቱ በመግለጽ ውድቅ አድርጎታል፡፡ በአጠቃላይ ተከሳሾቹ የኢትዮጵያን ሕግ፣ ሕገ መንግሥትና ኢትዮጵያ የተቀበለቻቸውን ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን የሚጥስ ድርጊት የፈጸሙ መሆናቸውን በመግለጽ ሁሉንም ጥፋተኛ ብሏቸዋል፡፡ ተከሳሾቹ የቅጣት ማቅለያቸውን፣ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ የቅጣት ማክበጃውን እስከ ሐምሌ 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በጽሕፈት ቤት በኩል እንዲያስገቡ በማዘዝ ፍርድ ለመስጠት ለሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ቀጥሯል፡፡

 

የባንኩ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ የተቀጡት በሌሉበት ነው

መንግሥታዊ ሰነዶችን በሐሰት በማዘጋጀት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሰባራ ባቡር ቅርንጫፍ፣ ከአምስት ሚሊዮን ብር በላይ ማጭበርበራቸው የተረጋገጠባቸው የቅርንጫፉ ሥራ አስኪያጅና ሁለት ግለሰቦች፣

ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ከአምስት እስከ 12 ዓመታት ከስድስት ወራት የሚደርስ ጽኑ እስራት ተፈረደባቸው፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ በሙስና ወንጀል ክስ የመሠረተባቸው፣ የቅርንጫፉ ሥራ አስኪያጅ አቶ መኳንንት አበጀ፣ ይፈመን ቲምበር ፕሮሰሲንግ የተባለ ድርጅት ተወካይ አቶ ብርሃኑ አዳፍሬና የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ይትባረክ አፈወርቅ ናቸው፡፡

የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ እንደሚያስረዳው፣ የባንኩ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ አቶ መኳንንት በ2005 ዓ.ም. የተለያዩ ሀሰተኛ የባንክ ዋስትና ሰነዶችን አዘጋጅተዋል፡፡ ያዘጋጁትን ሐሰተኛ ሰነድ ይፍመን ቲምበር ፕሮሰሲንግ ለተባለው ድርጅት በመስጠት ወንጀሉን መፈጸማቸውን ያስረዳል፡፡

በሥራ አስኪያጁ የተዘጋጀውን ሐሰተኛ ሰነድ የድርጅቱ ተወካይ አቶ ብርሃኑ በመቀበልና ሐሰተኛ የሽያጭ ዋስትና በማስያዝ፣ ከአንድ የማደያ ድርጅት ውል ተዋውለው 900,000 ብር የሚያወጣ የሞተር ዘይት፣ ቅባቶችና የነዳጅ ኩፖን ወስደው በወንጀሉ መሳተፋቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡

የይፈመን ቲምበር ፕሮሰሲንግ ሥራ አስኪያጅ ናቸው የተባሉት አቶ ይትባረክ፣ ከአቶ ብርሃኑ ጋር በመተባበር ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ላደረጉት የእንጨት ምሰሶዎች አቅርቦት ውል፣ ሐሰተኛ ሰነዱን በዋስትና በማቅረብ 4,908,623 ብር ቅድመ ክፍያ ከኢትዮ ቴሌኮም በቼክ መውሰዳቸውን ይገልጻል፡፡ ገንዘቡንም ወደ ድርጅታቸው አካውንት በማስገባትና አውጥተውም ለግል ጥቅማቸው ማዋላቸውም በክሱ ተጠቁሟል፡፡

የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ሦስቱም ተከሳሾች ድርጊቱን መፈጸማቸውን በምስክሮችና በሰነድ በማረጋገጡ፣ የባንኩ ሥራ አስኪያጅ አቶ መኳንንት በሌሉበት በስምንት ዓመታት ጽኑ እስራት፣ አቶ ብርሃኑ አዳፍሬ በ12 ዓመት ከስድስት ወራት ጽኑ እስራትና አቶ ይትባረክ አፈወርቅ በአምስት ዓመታት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 18ኛ ወንጀል ችሎት ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ሰጥቷል፡፡  

 

 

 

ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ነው ። ወ/ ሮ ሚልድሬድ ማሼጎ እና የአብራካቸው ክፋይ የሆነችው ፓትሪሲያ ስማቸው የአለማችን የድንቆች መዝገብ ውስጥ የሰፈረው። በደቡብ አፍሪካ ካስቲል ነዋሪ የሆኑት የ38 አመቷ እናት ወ/ሮ ማሼንጎና የ19 አመቷ ወጣት ልጃቸው ፓትሪሲያ በአንድ ወር ውስጥ፣ በአንድ ሣምንት ውስጥ እንዲሁም ከተመሳሳይ ሰው በመውለድ ወ/ሮ ማሼንጎ ልጅና የልጅ ልጅ አገኙ ፣ ወጣት ፓትሪሲያ ልጅና […]

ቴዲ አፍሮ ከጎሳዬ ጋር ተጣምረው ያቀርቡታል የተባለው ኮንሰርት በቪዛ ምክንያት ፕሮግራሙ መፋለሱ የሚታወስ ሲሆን ቴዲ ግን ዛሬ የበረራ ጉዞ ነበረው።ጉዳዩ ከሙዚቃ ስራ ጋር የተያያዘ አልነበረም።ባለቤቱ አምለሰት ሙጬ በአሁኑ ሰአት ለጤንነት ቼክሃፕ ኬንያ ናይሮቢ ትገኛለች።ቀደም ብላ የሄደችው ሚስቱን እንዴት ነሽ? ለማለትና ከጎኗ ለመሆን ፈልጎ ለጉዞ የሚያስፈልጉትን የነፍስ ወከፍ እቃዎች በሻንጣ በመሸከፍ በዛሬው አለት ከቀኑ 11 ሰአት […]

ህወሃት የሚመራዉ የመከላከያ ሰራዊት የዘመቻ መምሪያና ክትትል ቢሮ እንዲሁም የመከላከያ ደህንነት የበላይ ሃላፊዎች በአርበኞች ግንቦት 7 የከፈተበትን ጦርነት ለመከላከያ ሚኒስቴር በማመልከት በአስቸኳይ የመከላከያ ሐይል ተጨምሮ ስፍራዉን የመልሶ ማጥቃት የጦር ክልል ካላደረግነዉ በስተቀር የተዋጊዎቻችዉ የጦር ስልት ከባድና የሚያሰጋ መሆኑን ገልጿል። በመሆኑም የአርበኞች ግንቦት 7 ሰራዊት የከፈተዉን ጦርነት መልሶ ያጠቃል የተባለ ሐይል ከጎንደርና ከወሎ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን በሰሞኑ በተደረገ ጦርነት ብቻ የ 44 ተኛ […]

…ከዚህ በኋላ ህዝብ ሰብስቦ ማውራት ላቆም ነው ። ጊዜው ተቀይሯል.. ትግል ለደካማ መንፈስ አይሆንም ።ትግል መውደቅን ይጠይቃል። ሲወድቁ ግን ለመነሳት መሞከርን ይጠይቃል። ስንወድቅ ልታዩን ትችላላችሁ ስንነሳ ግን ታዩናላችሁ …Filed under: political opinion

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ የወንጀል ችሎት በእነ አቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ የአቃቤ ህግን እና የመከላከያ ምስክሮችን ቃል በንባብ አሰምቶ ማጠናቀቁን ተከትሎ ዛሬ በ18 ተከሳሾች ላይ ፍርድ ሰጥቷል። በዚህም መሰረት አቡበከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ፣ ካሚል ሸምሱ፣ በድሩ ሁሴን፣ ሼህ መከተ ሙሄ መኮንን፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሀመድ አባተ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ አቡበከር አለሙ፣ ሙኒር ሁሴን፣ ሼህ […]

የሽብረተኝነት ክስ የተመሠረተባቸው እነ አቡበከር መሐመድ ከሁለት ዓመት በላይ ጊዜ ከወሰደ ክርክር በኋላ በዛሬው ዕለት ጥፋተኛ ተባሉ፡፡

በፌዴራል ዓቃቢ ሕግ ክስ ተመሥርቶባቸው በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራተኛ ወንጀል ችሎት ከጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በተካሄደ ክርክር፣ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸውን የሰውም ሆነ የሰነድ ማስረጃዎች ማስተካከል አልቻሉም የተባሉት

አቡበከር መሐመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ፣ ከሚል ሸምሱ፣ በድሩ ሁሴን፣ ሼክ መከተ ሙሔ፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሐመድ አባተ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ካሊድ ሽኩር፣ አቡበከር ዓለሙ፣ ጉሩ ቱርኪ፣ ሼክ ባህሩ ኡመር፣ ሙኒር ሁሴን፣ ሼክ ሰኢድ፣ ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው፣ ሙባረክ አደም፣ እንዲሁም ካሊድ አብርሃም በዛሬው  ዕለት ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡

ተከሳሾቹ የተሰጠባቸውን የፍርድ ውሳኔ ከመቀመጫቸው በመነሳት በተደጋጋሚ  ተቃውመዋል፡፡ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ፍርድ ቤቱ ለሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ የሰጠ ሲሆን፣ ዓቃቤ ሕግ የቅጣት ማክበጃውን ተከሳሾች ደግሞ የቅጣት ማቅለያቸውን እስከ ሐምሌ 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በጽሕፈት ቤት በኩል እንዲያስገቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

«ወደ ዝዋይ ማረሚያ ቤት እንደተዘዋወርኩ ከጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ እና አበበ ቀስቶ ጋር ነበርን፡፡ ከጥቂት ጊዜያቶች በኋላ አበበ ቀስቶ ለህክምና ወደ አዲስ አበባ ሲዘዋወር ውብሸት ታዬ ወደ ሌላ ዞን ተቀየሯል፡፡ ዛሬ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በማንም እንዳይጎበኝ ተከልክሏል፡፡ እኔም ለተወሰኑ ወራት በማንም እንዳልጎበኝ እግድ ተጥሎብኝ እንደነበር ታውቃላችሁ፡፡ በኋላ ላይ ቤተሰቦቼ እና ወዳጆቼ እንዲጠይቁኝ ተፈቅዶ ነበር፡፡ ሰሞኑን ግን […]

  አፕሪል 18፣ 2012 ከሚላን የ”ሐኪንግ ቲም” ቢሮ የወጣው የክፍያ መጠየቂያ የተላከው ለኢንሳ (የመረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲ)ነው። ክፍያው የተፈጸመለት ሐኪንግ ቲም መቀመጫውን ጣልያን ያደረገ የኢንተርኔት ስለላ መሣሪያዎችና አግልግልቶችን የሚሰጥ ድርጅት ነው። ዜናው አክሎ እንደሚያተተው፣ ከመለስ ዜናዊ ሞት ከስምንት ወራት በኋላ ቢንያም ተወልደ የተባለ ግለሰብ ከመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን ጋራ ግንኙነት ያላቸው ስምንት ዶሜኖችን (የድረ ገጽ ስያሜና […]

አርበኞች ግንቦት 7 ጥቃት መሰንዘር መጀመሩን ዛሬ አስታወቀ። የአርባ ምንጭና አካባቢው ነዋሪዎች በወያኔ የፀጥታ ኃይሎችና ደህንነቶች ያልተቋረጠ እስር፣እና አፈና  እየተፈፀመባቸው መሆኑ ተገለፀ፡፡  ኢትዮጵያዊው ወታደር አልሸባብን መቀላቀሉ ተሰማ ብሀዴን መቢያስተዳድረው የአማራ ክልል  የተለያዩ ተቋማት ውጤት አልባ በመሆናቸው  እየፈረሱ መሆኑ ተነገረ በላይቤሪያ አዲስ በኢቮላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ለሁለተኛ ጊዜ ተገኙ።   አሰግድ ታመነ Filed under: NEWS, political […]

የኢትዬጵያ ቡና የተጫዋቾች ሰርቪስ የመጋጨት አደጋ ገጠመው ፡፡ የኢትዬጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ከ17 አመት በታች ቡድን ለጥሎ ማለፍ ዋንጫ ለዋንጫ ለማለፍ   ሰኔ 28/2007 ዓ.ም ከደደቢት ጋር ወሳኝ ግጥሚያ ነበረባቸው ፡፡ ይህን ተከትሎ ዛሬ ልምምዳቸውን በሱሉልታ ሜዳ አድርገው በሰርቪሱ ሲመለሱ ከቀኑ 4፡30 ሰዓት አካባቢ ወደ 18 ማዞሪያ የመኪና አደጋ አጋጥሟቸዋል ፡፡ በአደጋው ሶስት ተጫዋቾች ላይ […]

ከ1.9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበታል -የጋላፊንና የሚሌን ፍተሻ ጣቢያዎች ማለፉ ግርምት ፈጥሯል -ተጠያቂዎቹ ንግድ መርከብና የቻይና ድርጅት መሆናቸው ተጠቁሟል በትግራይ ክልል መቐለ ከተማ የሚገኘው አሚድአብ ጄኔራል ቢዝነስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ከቻይናው ዌይፋንግ ሹኦፌንግ ኢምፖርትና ኤክስፖርት ኩባንያ ገዝቶ ወደ ኢትዮጵያ ያስመጣው በአራት ኮንቴይነሮች የአኩሪ አተር ዘይት፣ ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. መቐለ ደረቅ ወደብ […]

ባለፉት ሦስት ቀናት የአርበኞች ግንቦት 7 ታጋዮች ትግራይ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች የወያኔን ሃይል ገጥመው የወያኔ መኮንኖችን ጨምሮ በርካታ የወያኔ ሰራዊት አባላትን እንደገደሉ በቃል-አቀባያቸው አማካኝነት ለኢሳት ቴሌቪዥን ገልጸዋል። ለጥቀውም እስከ ትላንት ድረስ ውጊያው ቀጥሎ እንደሚገኝ በድጋሜ ዜናውን አብስረዋል። በወያኔ ዘረኛና ግፈኛ አገዛዝ የተንገፈገፈው የኢትዮጵያ ህዝብም ጆሮውን አቅንቶ ሁኔታውን በመከታተል ላይ ነው። ቀድሞውንም የወያኔ ሥርዓት ያለ ሃይል […]

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና ፕሬዚዳንት ኦባማ በነዳጅ ማስተላለፊያ ግንባታ ላይ እንደሚወያዩ ታወቀ

ግዙፉ የአሜሪካ ኩባንያ ብላክ ስቶን ከጂቡቲ ኢትዮጵያ ድረስ የነዳጅ ማስተላለፊያ መስመር ለመገንባት በያዘው ዕቅድ ላይ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝና ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እንደሚወያዩ ምንጮች ገለጹ፡፡

በሐምሌ አጋማሽ ኢትዮጵያን ይጎበኛሉ ተብለው የሚጠበቁት ፕሬዚዳንት ኦባማ፣ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና ከኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ከሚወያዩባቸው በርካታ ጉዳዮች መካከል፣ የአሜሪካ ኩባንያዎች ኢትዮጵያ ውስጥ ለማካሄድ ያቀዷቸው ፕሮጀክቶች እንደሚገኙበት ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

ከእነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል ብላክ ስቶን ከጂቡቲ አዋሽ ድረስ ለመገንባት ያቀደው፣ 550 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የነዳጅ ማስተላለፊያ መስመር አንዱ እንደሆነ ታውቋል፡፡

ኩባንያው ይህንን ፕሮጀክት ለማካሄድ ቀደም ብሎ ምክረ ሐሳብ (ፕሮፖዛል) ለኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ አቅርቧል፡፡ ኢንተርፕራይዙ ከኩባንያው ጋር ሲደራደር ቢቆይም፣ መንግሥት በዚህ ጉዳይ ላይ አቅጣጫ መስጠት አለበት ተብሎ ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር አቅርቧል፡፡

ገንዘብ ሚኒስቴር ጉዳዩ ነዳጅ የማጓጓዝ በመሆኑ ከአዲስ አበባ ጂቡቲ ድረስ እየተገነባ ያለው የባቡር መስመር ከሚያጓጉዛቸው ሸቀጦች አንዱና ዋነኛው ነዳጅ ማመላለስ በመሆኑ፣ በዚህ ላይ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ አስተያየት እንዲሰጥ ምክረ ሐሳቡን ልኮታል፡፡

የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ የነዳጅ ማመላለሻ መስመሩ አዋጭ ስለመሆኑ እያጤነ መሆኑን፣ እስካሁን ቦርዱ ውሳኔውን እንዳላሳወቀ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ከጂቡቲ አዲስ አበባ ድረስ ናፍጣ፣ ቤንዚንና የአውሮፕላን ነዳጅ ለማጓጓዝ በተያዘው ፕሮጀክት 1.4 ቢሊዮን ዶላር ይፈልጋል ተብሎ ተገምቷል፡፡ ይህንን ገንዘብ ኩባንያው ከራሱና ከፋይናንስ ምንጮች የሚሸፍን ሲሆን፣ ፕሮጀክቱ እንዲሰጠው የሚፈልገውም በኮንሴሽን ነው፡፡

ኩባንያው እዚህ ሥራ ውስጥ ለመግባት የፈለገው በማደግ ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ፣ የነዳጅ ፍላጐቷ በየዓመቱ 15 በመቶ ዕድገት የሚያሳይ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡ ይህንንም ነዳጅ በየቀኑ 500 የነዳጅ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች በጠባብ መንገድ ላይ 800 ኪሎ ሜትር እየተጓጓዙ የሚያመላልሱ በመሆናቸው አዋጭነቱን በመገንዘብ ነው፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ይህንን ፕሮጀክት ቢፈልገውም፣ የባቡር መስመሩ በከፍተኛ ብድር በመገንባቱና ብድሩን ለመመለስ የግድ የአገሪቱ ነዳጅ በባቡር መመላለስ ይኖርበታል በሚል ምክንያት በጥልቀት መመርመር አስፈላጊ በመሆኑ እንዳዘገየው ምንጮች ይናገራሉ፡፡

ነገር ግን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ባለሙያዎች ግን፣ መንግሥት የአገሪቱ ነዳጅ በባቡርም፣ በነዳጅ ማስተላለፊያ መስመርም ቢጓጓዝ ጠቀሜታ ይኖረዋል ይላሉ፡፡

ምክንያቱን ሲያስረዱም በሁለቱም ማስተላለፊያ መስመሮች ነዳጅ ቢጓጓዝ የትራንስፖርት ዋጋ ላይ ውድድር ስለሚኖር ቅናሽ ይኖራል የሚል ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አንዱ ማጓጓዣ መስመር እንከን ቢገጥመው፣ በአንደኛው መጓጓዣ ዘዴ መጠቀም ስለሚቻል የፕሮጀክቶቹ መደራረብ ጥቅም እንጂ ጉዳት እንደሌለውም ያስረዳሉ፡፡

ብላክ ስቶን ይህንን ፕሮጀክት ለማከናወን ያቀደው በእህት ኩባንያው ብላክ ሬይ አማካይነት ሲሆን፣ ከዓመት በፊት በአጠቃላይ ጉዳዮች ላይ ከጂቡቲና ከኢትዮጵያ መንግሥታት ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል፡፡

የአሜካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ለጉብኝት አዲስ አበባ በሚመጡበት ወቅት፣ በዚህ ጉዳይ ላይ መንግሥታቸው የሚሰጠውን ድጋፍ በማስረዳት ድርድሩ ተቋጭቶ ወደ ሥራ ለመግባት ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና ከከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር እንደሚነጋገሩ ፕሮግራም መያዙን፣ ምንጮች ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡   

 

ከቻይና በኮንቴይነር ታሽጎ ወደ ኢትዮጵያ የተላከው ዘይት የድንጋይ ንጣፍ ሆኖ ተገኘ

ከ1.9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበታል

-የጋላፊንና የሚሌን ፍተሻ ጣቢያዎች ማለፉ ግርምት ፈጥሯል

-ተጠያቂዎቹ ንግድ መርከብና የቻይና ድርጅት መሆናቸው ተጠቁሟል

በትግራይ ክልል መቐለ ከተማ የሚገኘው አሚድአብ ጄኔራል ቢዝነስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ከቻይናው ዌይፋንግ ሹኦፌንግ ኢምፖርትና ኤክስፖርት ኩባንያ ገዝቶ ወደ ኢትዮጵያ ያስመጣው በአራት ኮንቴይነሮች የአኩሪ አተር ዘይት፣

ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. መቐለ ደረቅ ወደብ ደርሶ ሲከፈት ኮንክሪት የድንጋይ ንጣፍ ሆኖ ተገኘ፡፡

የሪፖርተር ምንጮች ከደረቅ ወደብ አስተዳደር የመቐለ ቅርንጫፍ እንደገለጹት፣ አሚድአብ ጄኔራል ቢዝነስ ከቻይናው ኩባንያ የገዛውን አራት ኮንቴይነሮች አኩሪ አተር ዘይት አጓጉዞ ወደ አገር ውስጥ እንዲያስገባለት፣ ከኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጋር ተስማምቷል፡፡ ድርጅቱም በገባው ውል መሠረት ሲአይኪው የተባለው የቻይና ድርጅት አረጋግጦና ሠርተፊኬት አሳይቶት ዕቃው መጫኑን ሰነዶች እንደሚያስረዱም ምንጮች ተናግረዋል፡፡ 

አሚድአብ ጄኔራል ቢዝነስ ዘይቱን ለሚልከው የቻይናው ኩባንያ እስከ ወደብ ማድረሻና የዘይቱን ዋጋ 67,860 ዶላር ከፍሏል፡፡ ለመርከብ ማጓጓዣ ደግሞ ከቻይና እስከ ጂቡቲ 7,684 ዶላር ከፍሏል፡፡ ከጂቡቲ እስከ መቐለ ደግሞ የማጓጓዣ 6,433.75 ዶላር ከፍሏል፡፡ በድምሩ 81,977.75 ዶላር ወይም 1,861,550.87 ብር መክፈሉን ምንጮች ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡ 

አራት ኮንቴይነር አኩሪ አተር ዘይት በኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክ አገልግሎት ድርጅት የደረቅ ጭነት ማጓጓዣ ተሽከርካሪ ተጭኖ መቐለ ደርሶ ሲከፈት፣ በኮንቴይነሮቹ ውስጥ የተጫነው ንፁህነቱ የተረጋገጠና የተመሰከረለት የአኩሪ አተር የምግብ ዘይት ሳይሆን፣ መንገድ ላይ የሚነጠፍ (በተለይ ለውኃ ማስተላለፊያ ቱቦዎች ከላይ ሽፋን የሚውል ጠፍጣፋና ረዘም ያለ መዝጊያ ድንጋይ) ኮንክሪት ንጣፍ ድንጋይ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ 

በሥፍራው የነበሩ የደረቅ ወደቡ ሠራተኞችም ሆኑ ስማቸው ያልተገለጸው የድርጅቱ ባለቤት ከመደንገጣቸው የተነሳ፣ ለደቂቃዎች በፀጥታ ውስጥ ሆነው እርስ በርስ ሲተያዩ መቆየታቸውን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡ 

ኤክስፖርት የሚያደርገው የቻይናው ኩባንያ ኮንቴይነሮቹን ሲወስድ ባዶ መሆናቸው ተረጋግጦና ማሸጊያ (ሲል) አብሮ እንደሚሰጠው የጠቆሙት ምንጮች፣ ኩባንያው ምርቶቹን በገባው ውል መሠረት ጥራታቸውን የጠበቁና ጉድለት እንዳይኖርም ሲአይኪው የሚባለው የጥራት ተቆጣጣሪ የቻይናው ድርጅት መከታተል እንደነበረበት፣ የመጫን ኃላፊነቱን የወሰደው የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክ አገልግሎት ድርጅትም ቁጥጥር ማድረግ ይገባው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ የመጫኛው ትዕዛዙ (ቢል ኦፍ ሎዲንግ) ዘይት ቢልም፣ ሲከፈት ግን ድንጋይ መሆኑን አክለዋል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ መንግሥት የተወከለው የቻይናው ሲአይኪው ድርጅት ተከታትሎ ማሳሸግና ማስጫን ሲገባው፣ የማይታወቅ ዕቃ እንዲላክ ማድረጉ ግራ እንዳጋባቸው ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ጊዜው አስፈሪ ከመሆኑ አንፃር፣ ማለትም አሸባሪ መላ ዓለምን እያሰጋ ባለበት ‹‹የተጫነው ዕቃ ፈንጂ ቢሆንስ?›› በማለት የሚጠይቁት ምንጮች፣ የድንጋዩ ጉዳይ ሕጉን ተከትሎ መፍትሔ የሚያገኝ ቢሆንም፣ መንግሥት ግን ችግሩን ሊፈትሽ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ 

ሌላው ምንጮችን ያስገረመው ኮንቴይነሮቹ የባህር ላይ ጉዞአቸውን ጨርሰው መቐለ ደረቅ ወደብ ከመድረሳቸው በፊት፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ቅርንጫፍ መፈተሻ ጣቢያዎች የጋላፊንና የሚሌን የፍተሻ ጣቢያዎች የመፈተሻ እስክሪን ውስጥ ሲያልፉ፣ የታየውን የዕቃ ዓይነት ሪፖርት አለማድረጋቸው ወይም እዚያው አለማስቆማቸው ነው፡፡ በስክሪን ውስጥ ስለሚታይ ጥብቅ ቁጥጥር አድርገው ቢሆን ኖሮ እዚያው ሊይዙት ይችሉ እንደነበር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ 

ዕቃውን ያስጫኑትን የአሚድአብ ጄኔራል ቢዝነስ ድርጅት ባለቤትን ለማግኘት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ ችግሩን የፈጠረው ወይም ቁጥጥሩን በአግባቡ ያልተከታተለው ማን እንደሆነ፣ በአስጫኙ ላይ ለደረሰው ኪሳራ ተጠያቂው ማን እንደሆነ፣ በተለይ ጥብቅ ቁጥጥር መደረግ ያለበት የባህር ላይ ትራንስፖርትን በሚመለከት ምን መደረግ እንዳለበት ማብራሪያ እንዲሰጥ የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅትን ለማነጋገር የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ በጋላፊና በሚሌ የፍተሻ ጣቢያዎች እንዴት ኮንቴይነሮቹ ሊያልፉ እንደቻለም ማብራሪያ ለመጠየቅ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንን የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊዎችን ለማግኘት የተደረገው ጥረትም እንዲሁ አልተሳካም፡፡ 

 

ለመርማሪዎች የይምሰል ጋብቻ ከመፈጸም እስከ ወንጀል ድርጊት መሳተፍ ይፈቅድላቸዋል

-የውጭ ሥራ ስምሪት አዋጅም ለፓርላማው ቀርቧል

ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመግታት ልዩ የምርመራ ቴክኒኮችን የሚፈቅድ ረቂቅ አዋጅ ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርላማ ቀረበ፡፡ 

ረቂቅ አዋጁ ‹‹ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና ስደተኞችን በሕገወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ 

ረቂቅ አዋጁ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ፣ ምክር ቤቱ ለሕግ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና ለማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር እይታ መርቶታል፡፡ የረቂቅ አዋጁ መፅደቅ በአስቸኳይ የሚፈለግ መሆኑ በአፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ የተገለጸ ሲሆን፣ ረቂቁ ፓርላማው ማክሰኞ ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. የሥልጣን ዘመኑን ከማብቃቱ በፊት ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ 

ረቂቅ አዋጁ በሃምሳ አንቀፆችና በሰባት ምዕራፎችም የተከፋፈለ ነው፡፡ ምዕራፎቹም ጠቅላላ ድንጋጌዎችን፣ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና ስደተኞችን በሕገወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀሎችን፣ የመከላከል፣ የምርመራ፣ የክስና የማስረጃ ሥነ ሥርዓት ድንጋጌዎችን፣ የተጎጂዎችን ጥበቃ፣ መልሶ ማቋቋምና ካሳ፣ ስለፈንድ መቋቋም፣ የባለድርሻ አካላት ትብብርና ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችን የያዘ ነው፡፡ 

ረቂቅ አዋጁ በኢትዮጵያ በጥብቅነቱና አወዛጋቢነቱ ከሚታወቀው የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ ሁሉ እጅግ የጠበቀ የሚያደርጉ አንቀጾችን ይዟል፡፡ ከዚህ ውስጥ አንዱና በዋነኝነት የሚጠቀሰው ልዩ የምርመራ ዘዴዎችን ስለመጠቀም የሚፈቅደው አንቀጽ 18 ይገኝበታል፡፡ 

ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና ስደተኞችን በሕገወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀሎች በባህሪያቸው በቡድን የሚፈጸሙ በመሆናቸው፣ የወንጀል ድርጊቱ ከአንድ አገር በላይ በተደራጀ የወንጀል ቡድን የሚፈጸም በመሆኑ፣ በተለይም ከምልመላ ጀመሮ እስከ መጨረሻው ሒደት ያለው የወንጀሉ አፈጻጸም በቅብብሎሽና በቅንጅት የሚሠራ በመሆኑ፣ በዚህ ወንጀል ውስጥ የሚሳተፉ ተጠርጣሪዎችን በተሟላ ሁኔታ ለመያዝ መደበኛውን የምርመራ ሒደት መጠቀም አዋጭ እንዳልሆነ የረቂቅ አዋጁ ማብራሪያ ያስረዳል፡፡ 

እነዚህን ወንጀሎች ከሥር ከመሠረታቸው ለመረዳትና በወንጀል ድርጊት አፈጻጸሙ የሚሳተፉ ሰዎችን ማንነት፣ የወንጀሉን ማስረጃ፣ የአፈጻጸም ሥልት፣ የሚፈጸምበትን ሁኔታና ጥቅም ላይ የዋሉ የጉዞ አቅጣጫዎች በአግባቡ ለማወቅና በመረጃ ላይ የተመሠረተ የምርመራ ሒደትን ለማከናወን ልዩ የምርመራ ዘዴዎች መጠቀም እንደሚያስፈልግ ማብራሪያው ያስረዳል፡፡ 

ከእነዚህም ቴክኒኮች መካከል ሰርጎ የመግባት ማለትም በአንድ የተደራጀ የዚህ ወንጀል ቡድን ውስጥ ራሱን የዚያ ድርጊት ደጋፊ በማድረግ፣ በወንጀል ቡድኑ ውስጥ አባል በመሆን መረጃዎችንና ማስረጃዎችን ማሰባሰብ ይገኝበታል፡፡ 

ሌላኛው ደግሞ በድብቅ ክትትል ማድረግ ወይም ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎችን ቢያንስ በሁለት ዓይነት መንገድ ክትትል ማድረግን እንደሚመለከት ማብራሪያው ይገልጻል፡፡ አንደኛው ዘዴ ተጠርጣሪው ላይ በአካል የሚደረግ ክትትልና መረጃ የመሰብሰብ ሒደት ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ እንደ አመቺነቱ የሚኖርበትን አካባቢ፣ ቤት፣ የሥራ ቦታ፣ ወዘተ በድብቅ የስለላ ካሜራዎች በመጠቀም እንቅስቃሴውን የመከታተል ሒደት ነው፡፡ ሌላኛው የምርመራና መረጃ የመሰብሰብ ዘዴ ደግሞ የይምሰል ግንኙነት መፍጠርን የሚመለከት ነው፡፡ ‹‹የይምሰል ግንኙነት ማለት በሕግ ውጤት የሌለው ነገር ግን በወንጀል ድርጊቱ የሚሳተፉ አካላት ላይ ማስረጃ ለማሰባሰብ የሚረዳ ግንኙነት ሲሆን፣ ለምሳሌ የወንጀል ቡድኑ ወንጀሉን ለመፈጸም ገንዘብ የሚያስፈልገው መሆኑ ከታወቀ ቀድሞ ከጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በሚገኝ ፈቃድ አንድ ሰው የወንጀል ድርጊቱን በገንዘብ እንዲረዳ በማድረግ ማስረጃ ማሰባሰብ›› መሆኑን የረቂቁ አባሪ ማብራሪያ ይገልጻል፡፡ 

ሌሎች ዓይነቶችን የይምሰል ግንኙነቶችን መፍጠር እንደሚቻልም ማብራሪያው ያትታል፡፡ ከእነዚህም መካከል ‹‹ከተጠርጣሪዎች ጋር ጋብቻ መፈጸም››፣ ‹‹የንግድ ተቋም በጋራ መመሥረት››፣ ወዘተ ሊያጠቃልል የሚችል ሲሆን፣ ዋነኛ ዓላማው ከሌሎች ወገን ወንጀሉን አስመልክቶ መረጃ ለማግኘት ታሳቢ ተደርጎ የሚፈጠር ግንኙነት እንደሆነና በሕግ ፊት ተጠያቂነትን እንደማያስከትል ይገልጻል፡፡

አንድ መርማሪ ሠርጎ በገባበት የወንጀል ቡድን ውስጥ አባልነቱን እንዲቀበሉት፣ የወንጀል ቡድኑ አባላት ይህንን ሠርጎ ገብ መርማሪ በግልጽ ወንጀል እንዲፈጽም ሊያደርጉት እንደሚችሉ የሚያትተው የረቂቅ አዋጁ ማብራሪያ፣ መርማሪው በተግባር ወንጀል እየፈጸመ ቢሆንም ዓላማው ማስረጃ ለማሰባሰብ በመሆኑ በወንጀል እንደማይጠየቅ ያስረዳል፡፡ 

ለዚህም ሲባል መርማሪው አስቀድሞም የወንጀል ነፃ ስምምነት መፈራረም እንደሚኖርበትና ይህን የወንጀል ነፃ መብት አለ በሚል ግን ግድያ ከመፈጸም፣ አስገድዶ መድፈር የመሳሰሉት ከባድ ወንጀሎች መፈጸም እንደሌለበት ያብራራል፡፡ 

ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና ስደተኞችን በሕገወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀል ማለት፣ በአገር ውስጥ ሥራና ሠራተኛን ለማገናኘት ወይም ለሥራ፣ ለሥራ ልምምድ ወደ ውጭ አገር መላክ በሚል ሽፋን የሚፈጸም፣ በጉዲፈቻ ስምምነት በማድረግ ወይም በጉዲፈቻ ሽፋን፣ ወይም በሌላ ማንኛውም መንገድ ለምሳሌ ዛቻን፣ ኃይልን፣ ጠለፋን፣ ማታለልን፣ የተስፋ ቃልን፣ ስለሌላው ኃላፊነት ያለበትን ሰው ፈቃድ ለማግኘት በመደለል፣ ጥቅም በመስጠት ሰዎችን የመመልመል፣ የማጓጓዝ፣ የማዘዋወር፣ የማስጠለል፣ የመቀበል ወንጀል መሆኑን ረቂቅ አዋጁ ይገልጻል፡፡ 

ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርን እያወቀ ወይም ማወቅ ሲገባው የራሱንም ሆነ በይዞታው ሥር ያለውን ቤት፣ ሕንፃ ለሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ዓላማ ያከራየ፣ እንዲጠቀሙ የፈቀደ ወንጀሉን በመደገፍና በማመቻቸት ተጠያቂ እንደሚሆን ይገልጻል፡፡ 

በተፈጸመ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ድርጊት በተጎጂው ላይ ከፍተኛ የአካል ጉዳት ወይም ሞት ያስከተለ እንደሆነ ወንጀል አድራጊው ድርጊቱን የፈጸመው በተደራጀ የወንጀል ቡድን አባል በመሆን፣ ቡድኑን በመምራት ወይም በማስተባበር እንደሆነ ወይም ወንጀሉ የተፈጸመው በብዛትና በስፋት ከሆነ ቅጣቱ የዕድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም ሞት እንደሚሆን በረቂቁ ተካቷል፡፡

በዚህ ወንጀል ዓይነት ላይ ይርጋ እንደማይኖር የተቀመጠ ሲሆን፣ ማንኛውም ሰው ወንጀል መፈጸሙን ወይም ሊፈጽም መሆኑን የሚያውቅ ማንኛውም ሰው ለሕግ አካል የማሳወቅ ግዴታ ተጥሎበታል፡፡ በተመሳሳይም ለዚህ የወንጀል ድርጊት ዓላማ የቤተሰቡ አባል የሆነ ሰው ከመደበኛ የመኖሪያ አካባቢው የጠፋ መሆኑን ያወቀ ከሆነ፣ ወዲያውኑ ለሕግ አካል እንዲያሳውቅ ረቂቁ ያስገድዳል፡፡ በዚህ ረቂቅ አዋጅ መሠረት የተከሰሰ ሰው ወንጀሉን ስላለመፈጸሙ ለፍርድ ቤት የማስረዳት ሸክም እንደሚወድቅበትም ይደነግጋል፡፡ 

ይህ በእንዲህ እንዳለ በተመሳሳይ እጅግ በጣም ጥብቅ የሆነ የኢትዮጵያ የውጭ አገር ሥራ ስምሪት ረቂቅ አዋጅም ለፓርላማው ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ቀርቧል፡፡ በዚህ ረቂቅ አዋጅ መሠረት ወደ ውጭ አገር በቤት ሠራተኝነት ለመሄድ ቢያንስ የስምንተኛ ክፍል ደረጃ ሊኖር እንደሚገባና ይህንኑም በማስረጃ ማስደገፍን ይጠይቃል፡፡ በተጨማሪም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ መያዝ የሚያስፈልግ ሲሆን፣ በሠራተኝነት መሄድ የሚቻለው ኢትዮጵያ የሁለትዮሽ ስምምነት ያደረገችባቸው አገሮች ብቻ ነው፡፡ 

በዚህ የሥራና ሠራተኛ የማገናኘት ሥራ ላይ ለመሰማራት የሚፈልጉ ኤጀንሲዎች በግለሰብ ደረጃ ከሆነ አንድ ሚሊዮን ብር ካፒታል እንደሚያስፈልግ፣ በአክሲዮን ደረጃ ከሆነ ደግሞ አምስት ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ ረቂቁ ያስረዳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ማንኛውም ኤጀንሲ ለሠራተኛው መብትና ደኅንነት ዋስትና ማስከበሪያ የሚውል 100,000 ዶላር ወይም ተመጣጣኙን የኢትዮጵያ ብር በዝግ ሒሳብ በባንክ እንዲያስቀምጥ ይገደዳል፡፡ 

እንዲሁም ሠራተኛን የሚቀጥር አካል ሠራተኞች በሥራ ውል መጣስ ምክንያት የሚያነሱትን የገንዘብ ክፍያ ጥያቄዎች መሸፈን እንዲቻል፣ የውጭ አሠሪዎች የዋስትና ፈንድ እንደሚቋቋምና ለዚሁ ይረዳ ዘንድ እያንዳንዱ ቀጣሪ ለአንድ ሠራተኛ 50 ዶላር ወደ ፈንዱ እንዲያስገባ ይገደዳል፡፡ 

ይህ አዋጅ በተጠናቀቀው የፓርላማው የሥልጣን ዘመን ይፀድቃል ተብሎ የማይጠበቅ ቢሆንም፣ የፓርላማው የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በጋራ እንዲያዩት ተመርቶላቸዋል፡፡ 

 

የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ባለፈው ዓመት ክረምት ተከስቶ የነበረው ዓይነት የስኳር ዕጥረት እንዳያጋጥም፣ በቀናት ውስጥ ከውጭ የገዛውን አንድ ሚሊዮን ኩንታል ወደ አገር ውስጥ እንደሚያስገባ አስታወቀ፡፡

ከውጭ እንደሚገባ ከሚጠበቀው ስኳር በተጨማሪ፣ በሙከራ ምርት ላይ የሚገኙት የተንዳሆና የከሰም ስኳር ፋብሪካዎችም ምርታቸው እንደሚያቀርቡ፣ የኮርፖሬሽኑ የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊ አቶ ዘመድኩን ተክሌ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

አቶ ዘመድኩን እንደሚሉት፣ በጥቂት ቀናት ውስጥ የሚገባው የስኳር ምርት በአገር ውስጥ ያሉ ፋብሪካዎች በክረምቱ ምክንያት ምርት ቢያቆሙ እንኳ፣ ቅድመ መጠባበቂያ እንዲሆን ከዱባይ የተገዛ ነው፡፡

በተለይ የመተሐራና የወንጂ ስኳር ፋብሪካዎች እስካሁን እያመረቱ ቢሆንም፣ በክረምቱ ምክንያት የሸንኮራ አገዳ አቅርቦት ዕጥረት እንደሚያጋጥም ይጠበቃል፡፡

ይሁን እንጂ በመኩራ ምርት ላይ ያሉት የተንዳሆና የከሰም ፋብሪካዎች የክረምቱ ዝናብ ብዙም ተፅዕኖ ስለማያደርግባቸው፣ በመጠኑም ቢሆን እንደሚያመርቱ ኃላፊው አስረድተዋል፡፡

የወንጂ ስኳር ፋብሪካ የማምረት አቅሙን ወደ 2.2 ሚሊዮን ቶን ለማድረስ ማቀዱን በቅርቡ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ የፋብሪካው ኃላፊዎች እንደገለጹት፣ በተለይ የሸንኮራ ምርት አሁን ካለው ከአምስት ሺሕ ሔክታር ወደ 12,500 ሔክታር ለማሳደግ ታቅዷል፡፡

በከፊል የሙከራ ምርት ከጀመሩት ውስጥ የተንዳንሆና የኩራዝ ስኳር ፋብሪካዎችም ከሦስት እስከ ስድስት ወራት ባለው ጊዜ ውስጥ እንደሚጀምሩ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩን ጠቅሰን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ የከሰም ስኳር ፋብሪካ በቀን እስከ 10,000 ቶን አገዳ የመፍጨት አቅም እንዳለው የገለጹት ሚኒስትሩ አቶ አህመድ አብተው፣ ሆኖም በአሁኑ ወቅት 6,000 ቶን አገዳ በቀን በመፍጨት ሙከራ እንደሚጀምር አስታውቀዋል፡፡

 እንደ ስኳር ኮርፖሬሽን መረጃ ከሆነ፣ የከሰም ስኳር ፋብሪካ በ20,000 ሔክታር መሬት ላይ የተንጣለለና በመስኖ ውኃ የሚለማ የአገዳ እርሻ አለው፡፡ ሥራ በሚጀምርበት ወቅት 153 ሺሕ ቶን ስኳር፣ 12,500 ሜትር ኩብ ኤታኖል በዓመት እንደሚያመርት የሚጠበቅ ፕሮጀክት ነው፡፡ በሙሉ አቅሙ ማምረት ሲጀምር 260 ሺሕ ቶን ስኳርና 30,000 ሜትር ኩብ ኢታኖል፣ እንዲሁም 15 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ያመነጫል ተብሎም ይጠበቃል፡፡  

 

የሰማያዊ ፓርቲ የዞን አመራር ገድሏል የተባለው ግለሰብ በጽኑ እሥራት ተቀጣ

‹‹ይህ ራስን ማታለልና አገርን ማዋረድ ነው›› የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር

‹‹ቅጣቱ የተሰጠው በፖሊስ ከተጣራና ፍርድ ቤቱም በምስክሮች ካረጋገጠ በኋላ ነው›› የአማራ ክልል መንግሥት

በአማራ ክልል በምሥራቅ ጎጃም ደብረ ማርቆስ ከተማ ውስጥ ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. የተገደለው የሰማያዊ ፓርቲ የዞን አመራርና የሕግ ባለሙያው የአቶ ሳሙኤል አወቀ ገዳይ ነው የተባለ ግለሰብ፣ በ19 ዓመታት ጽኑ እሥራት እንዲቀጣ ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ተሰጠ፡፡ 

 

ፍርዱን የሰጠው የምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ማርቆስ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሲሆን፣ ሰኔ 8  ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 1፡30 ሰዓት አካባቢ ግድያውን መፈጸሙ በምስክሮች ተረጋግጧል የተባለው ፍርደኛ ተቀበል ገዱ ይባላል፡፡ 

የፓርቲው የዞን አመራር አቶ ሳሙኤል በተገደለበት ወቅት የክልሉ መንግሥት በሰጠው መግለጫ፣ አቶ ሳሙኤል የተገደለው ጥብቅና ቆሞለት ከነበረ አርሶ አደር ጋር በፈጠሩት አለመግባባት እንደነበር ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ ገዳዩ የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ሲጠይቀው፣ በደብረ ማርቆስ ከተማ ቤት ተከራይቶ የቀን ሥራ እየሠራ ቤተሰቦቹን የሚያስተዳድር መሆኑን በመግለጽ ቅጣቱ እንዲቀልለት ማመልከቱ ተነግሯል፡፡ በመሆኑም ገዳይ መሆኑ የተረጋገጠበት ፍርደኛ፣ ከአርሶ አደርነት እንዴት የቀን ሠራተኛ ሊሆን እንደቻለ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ግራ መጋባታቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ 

የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በዕለቱ በችሎት ከተገኙት ቤተሰቦቹና የችሎቱ ታዳሚዎች እንደተረዱት፣ የወንጀሉ አፈጻጸም አልተገለጸም፡፡ ገደለ የተባለው ግለሰብ ሟችን አያውቀውም ብለው፣ በወቅቱ ወንጀሉን አብረው የፈጸሙ ተባባሪዎች እንዳልተያዙ የተገለጸ ቢሆንም፣ ክትትል ተደርጎ የእነሱ መያዝና አለመያዝ ሳይረጋገጥ፣ በጥድፊያ የቅጣት ውሳኔ መስጠቱ በራሱ የሚያሳየው ነገር እንዳለ አስረድተዋል፡፡ 

የፓርቲያቸው አባል የተገደለበት ሁኔታ የተቀነባበረና ሊድበሰበስ የማይችል መሆኑን የሚገልጹት ሊቀመንበሩ፣ የወንጀል ሒደቱ በትክክል እንዳልተጣራ ፍርድ ቤቱ እንኳን ከሰጠው ፍርድ መረዳት እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡ 

ሟች አቶ ሳሙኤል አወቀ እነማን እየተከታተሉት እንደሆነ፣ ሊገደል እንደሚችል፣ እሱ ቢሞትም ትግሉ እንደሚቀጥል ጽፎና አሳውቆ መሞቱን የጠቆሙት ኢንጂነር ይልቃል፣ አንድ ሰው የማያውቀውን ሰው ሊገድል እንደማይችል ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተፈጸመው ድርጊት ራስን ማታለልና አገርን ማዋረድ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ቤተሰቦቹና ሕዝቡ በጣም ማዘናቸውንም አክለዋል፡፡ 

ገዳይ ተቀበል ገዱ ወንጀሉን ሲፈጽም የአካባቢው ነዋሪዎች ጮኸው እጅ ከፍንጅ እንደያዙት የገለጹት ደግሞ፣ የአማራ ብሔራዊ ክልል መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ንጉሡ ጥላሁን ናቸው፡፡ 

በፖሊስ ተጣርቶና ፍርድ ቤቱ በምስክሮች አረጋግጦ ተገቢ ነው ያለውን ቅጣት መወሰኑን የገለጹት ኃላፊው፣ አንዳንድ ወገኖችና የፓርቲው አመራሮች ግድያውን ከፖለቲካ ጋር ለማገናኘት የሚያደርጉት ጥረት ተገቢነት እንደሌለው አስታውቀዋል፡፡ 

ጉዳዩን ከምርጫ ጋር ለማያያዝ ቢሞከርም ሁሉም ነገር ከተጠናቀቀ በኋላ የተፈጸመ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ንጉሡ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በምርጫው ያጣውን የኅብረተሰቡን ውሳኔ (ድምፅ) ወደጎን በመተው ሰበብ እየፈለገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ሰላማዊውን ሕዝብ ሰላም ለመንሳትና የእርስ በርስ ቅራኔ ለመፍጠር ካልሆነ በስተቀር፣ ወንጀሉን የፈጸመው አካል በምስክር ተረጋግጦበት ቅጣቱን ማግኘቱን አስረድተዋል፡፡ ገዳይ በደብረ ማርቆስ ከተማ ቤት ተከራይቶ የቀን ሥራ በመሥራት ወንድሞቹን እንደሚያስተዳድር አቶ ንጉሡም አረጋግጠዋል፡፡ 

የደብረ ማርቆስ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በሰጠው የጽኑ እሥራት ቅጣት ላይ አስተያየት የሰጡ ደግሞ፣ ድርጊቱ በተፈጸመ በ17 ቀናት ውስጥ የቅጣት ውሳኔ መሰጠቱ ጥሩ ቢሆንም፣ ተመሳሳይ ወንጀል ፈጽመው ለዓመታት ውሳኔ ሳይሰጥባቸው በየማረሚያ ቤቱ ያሉትን ተጠርጣሪዎች ሲያስቡ ግን፣ ጥርጣሬ እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡ አንድ ሰው በወንጀል ተጠርጥሮ ሲታሰር፣ ፖሊስ ተጨማሪ ምርመራ ለማድረግ ዝቅተኛ የሚጠይቀው የምርመራ ጊዜ 14 ቀናት በተለመደበት ሁኔታ፣ ይኼኛው የክስ ሒደት በ17 ቀናት ውስጥ መፈጸሙ ግራ እንዳጋባቸው ተናግረዋል፡፡ አቶ ንጉሡ ግን ወንጀለኛው እጅ ከፍንጅ የተያዘና ሁሉም ማስረጃ በአንድ ጊዜ በአጭር ቀናት በመሟላቱ፣ ተገቢ ውሳኔ መሰጠቱን ገልጸው አስተያየት ሰጪዎቹን ተቃውመዋል፡፡ 

 

ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ለመልካም አስተዳደር ዕጦትና ለሙስና ትኩረት እንዲሰጥ ተጠየቀ

ሰሞኑን ለውይይት የቀረበው ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በርካታ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ቢያቅፍም፣ ሙስናና የመልካም አስተዳደር እጦት ሥጋት እንደሆነበት ተገለጸ፡፡ 

ከአብዛኛዎቹ ተሰብሳቢዎች ጐልተው የተነሱ ነጥቦች ይህንን ግዙፍ ብሔራዊ ዕቅድ ለመተግበር፣ ቅድሚያ የመልካም አስተዳደርና የሙስና ጉዳዮች መፍትሔ ሊያገኙ እንደሚገባ የሚገልጹ ናቸው፡፡ 

አስተያየት ሰጪዎቹ እንደሚሉት፣ በአዲስ አበባና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች የመልካም አስተዳደር እጦት ተባብሷል፡፡ ሙስና የዕለት ተዕለት ክስተት እየሆነ መምጣቱ በምሬት ተገልጿል፡፡

መንግሥት የቀረፀው የዚህ ግዙፍ ፕሮጀክት ስኬት በቀጥታ ከመልካም አስተዳደር ጋር የሚገናኝ በመሆኑ፣ አገርን በማዳን አስተሳሰብ ላይ የተመሠረተ ዕርምጃ ሊወሰድ ይገባል በማለት አስተያየት የሰጡ በርካታ ናቸው፡፡

ከጥቂት ቀናት በኋላ የሚጠናቀቀው የመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ይዞ መቅረቡ ይታወሳል፡፡ 

ከእነዚህ መካከል አሥር የስኳር ፕሮጀክቶች፣ ከሁለት ሺሕ ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍን አዲስ የባቡር መስመር ግንባታ፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብና የማዳበሪያ ፋብሪካዎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ 

በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ እነዚህ ፕሮጀክቶች ተስፋፍተው እንደሚቀጥሉ፣ ቀደም ባለው ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ ያልነበሩ የፔትሮሊየምና የኬሚካል ፋብሪካዎች ይገነባሉ ቢባልም፣ ከመጀመሪያው ዕቅድ ተነጥሎ ሊታሰብ የሚያስችለው ዓይነተኛ መለያ የለውም ተብሏል፡፡

ይህ ሐሳብ ባለፈው ረቡዕና ሐሙስ በአዲስ አበባ ባህልና ቴአትር አዳራሽ በተካሄደው የዕቅድ ሰነድ ውይይት፣ የኢሕአዴግ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩትና በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት የአንድ ክፍል ኃላፊ የሆኑት አቶ ሴኮቱሬ ጌታቸው በሰጡት አስተያየት፣ የመጀመሪያው ዕቅድ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ይዞ በመቅረቡ ብሔራዊ መነሳሳት ፈጥሯል ብለው፣ የአሁኑ ዕቅድ ፕሮጀክቶችን ቢይዝም ከመጀመሪያው ዕቅድ ጋር በግልጽ የተቀመጠ ልዩነት የለውም በማለት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ 

‹‹እኛ የምንከተላቸው ልማታዊ መንግሥታት አንድ ዕቅድ አጠናቀው ሌላ ሲያቅዱ ልዩነቱ በግልጽ ይታያል፤›› በማለት የተናገሩት አቶ ሴኮቱሬ፣ ‹‹እኛም ብሔራዊ መነሳሳት ለመፍጠር ልዩነቱን በግልጽ በማውጣት ብሔራዊ ግብ ልናስቀምጥ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ሴኮቱሬ ቢካተቱ ያሏቸውን ሐሳቦችም ሰንዝረዋል፡፡ ከሰነዘሯው ሐሳቦች ብሔራዊ አገልግሎት አንዱ ነው፡፡ ‹‹በወታደራዊው መንግሥት የሥልጣን ዘመን ብሔራዊ ውትድርና መጥፎ ጠባሳ ጥሎ ቢያልፍም፣ በአሁኑ ወቅት በሩቁ ከምንሸሸው በበጐ ጐኑ ልንጠቀምበት ይገባል፤›› ካሉ በኋላ፣ በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ከመመረቃቸው በፊት ለተወሰኑ ጊዜያት ወደመጡበት ኅብረተሰብ ተመልሰው እንዲያገለግሉ ቢደረግ ጥቅሙ የጐላ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ‹‹ይህ ሁኔታ ኅብረተሰቡን ከመጥቀሙ ባሻገር ተማሪዎቹ ከፍተኛ ዕውቀት የሚያገኙበት ይሆናል፡፡ በአገራቸው እንዲኮሩም ያደርጋል፤›› ብለዋል፡፡ 

ስብሰባውን ይመሩ የነበሩት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ለአቶ ሴኮቱሬ አስተያየት ምላሽ ሲሰጡ፣ የብሔራዊ አገልግሎት ጉዳይ እንደ ስትራቴጂ ሊወሰድ ይችላል ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ይበልጥ በመነጋገር የሚያዋጣውን ማየት ይቻላል ካሉ በኋላ፣ በኢትዮጵያ ይህንን ጉዳይ መተግበር አዋጭ ስለመሆኑ ከባህልና ከታሪክ አንፃር መርመር ያስፈልጋል በማለት አክለዋል፡፡ አቶ ድሪባ ጉዳዩ ከኢሕአዴግ መስመር ጋር ያለውን ልዩነትም አስረድተዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ የምትከተላቸው ሌሎች አገሮች ልማታዊ መንግሥት ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ግን ልማታዊ ዴሞክራሲን የምትከተል በመሆኑ ጉዳዩን በጥልቀት ማየት ያስፈልጋል፤›› በማለት አቶ ድሪባ ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በተካሄደው ስብሰባ አብዛኛዎቹ ተሰብሳቢዎች በትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ጥልቅ ሐሳቦች ላይ አስተያየት ከመሰንዘር ይልቅ፣ ብዙም ግንኙነት በሌላቸው የዕለት ተዕለት ጉዳዮች ላይ አስተያየት ሲሰጡ ተስተውለዋል፡፡

በዚህ ጉባዔ የአምስት ዓመቱን ዕቅድ ያቀረቡት በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ጌታቸው አዳም ሲሆኑ፣ ከአቶ ድሪባ ጋር መድረኩን የመሩት የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበው ናቸው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ 192 ገጽ ያለው ሲሆን፣ ለውይይት የቀረበው በ65 ገጽ ተጨምቆ መሆኑን አቶ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡    

 

ሚድሮክ ጐልድ ምንም ዓይነት የመንግሥት ዕዳ የለብኝም አለ

ዋና ኦዲተር ማስተባበያውን አጣጥሎታል 

የፌዴራል ዋና ኦዲተር በሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ ለፓርላማ ባቀረበው ሪፖርት፣ የማዕድን ሚኒስቴር የሼክ መሐመድ አል አሙዲ የወርቅ ልማት ኩባንያ ከሆነው ሚድሮክ ጐልድ በሕግ የተወሰነውን ገቢ ባለመሰብሰቡ

፣ አገሪቱ ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ አጥታለች ማለቱን የኩባንያው ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር አርጋ ይርዳው ‹‹ፍፁም ሀሰት›› ነው ሲሉ አስተባበሉ፡፡ ዋና ኦዲተር ገመቹ ዱቢሶ በበኩላቸው፣ የሚድሮክ ጐልድን ማስተባበያ በማጣጣል ማዕድን ሚኒስቴር ያልሰበሰበውን የመንግሥት ገንዘብ አሁንም ገቢ ሊያደርግ ይገባል ብለዋል፡፡

በማዕድን አዋጁ 78/2002 መሠረት በከፍተኛ የማዕድን አምራቾች ላይ ስምንት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ፣ እንዲሁም በከፍተኛ የማዕድን አምራች ኩባንያዎች ላይ መንግሥት አምስት በመቶ ነፃ የአክሲዮን ድርሻ እንደሚኖረው ቢደነገግም፣ የማዕድን ሚኒስቴር ከ2004 እስከ 2006 ዓ.ም. ባሉት የበጀት ዓመታት ከሚድሮክ ጐልድ የሰበሰበው የሮያሊቲ ክፍያ አምስት በመቶ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ እንዲሁም ከመንግሥት ነፃ የአክሲዮን ድርሻ ሁለት በመቶ ብቻ መሆኑን በማዕድን ሚኒስቴር ላይ በተካሄደው የክዋኔ ኦዲት ቁጥጥር መረጋገጡን ዋና ኦዲተሩ ለፓርላማ ሪፖርት አድርገዋል፡፡ ፓርላማው ካፀደቀው የሮያሊቲና የመንግሥት ድርሻ ምጣኔ ውጪ ሚኒስቴሩ ሚድሮክ ጐልድን በዝቅተኛ ምጣኔ በማስከፈሉ፣ በድምሩ 429 ሚሊዮን ብር ገቢ መንግሥት ማጣቱን ሪፖርት በማድረግ ማዕድን ሚኒስቴር በአገሪቱ ሕግ መሠረት ገቢዎችን እንዳልሰበሰበ ገልጿል፡፡ 

ሪፖርተር ይህንን የዋና ኦዲተሩን የኦዲት ሪፖርት መሠረት በማድረግ በሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ዕትሙ ዘገባ ያቀረበ መሆኑ ይታወሳል፡፡ የሚድሮክ ጐልድ ዋና ሥራ አስኪያጅና የሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር አረጋ ይርዳው ለሪፖርተር በላኩት ደብዳቤ፣ ‹‹ኩባንያው ሕግን አክብሮ ኃላፊነቱን የሚወጣ ድርጅት ነው፡፡ አሥር ሳንቲም የመንግሥት ዕዳ የለበትም፤›› ብለዋል፡፡

ሚድሮክ ጐልድ የማዕድን አዋጅ ቁጥር 52/1985 መሠረት በማድረግ ከማዕድን ሚኒስቴር ጋር የ20 ዓመታት የማዕድን ማውጣት ውል መግባቱን፣ በውሉ መሠረትም አምስት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያና ሁለት በመቶ ነፃ የአክሲዮን ድርሻ በኩባንያው ላይ እንዲኖረው መደረጉን በደብዳቤያቸው አብራርተዋል፡፡

ውሉ መሠረት ያደረገበት የማዕድን አዋጅ በአዋጅ ቁጥር 678/2002 ተሻሽሎ በሐምሌ ወር 2002 ዓ.ም. ሥራ ላይ መዋሉን የሚያስታውሰው የዶ/ር አረጋ ደብዳቤ፣ በዚህ አዋጅ ላይ የሮያሊቲ ክፍያ ወደ ስምንት በመቶ እንዲያድግ፣ የመንግሥት ነፃ ድርሻ ሁለት በመቶ እንዲሆንና ለወርቅ ማምረት ሥራ የቀረጥ ነፃ መብት እንዳይፈቀድም መከልከሉን ገልጸዋል፡፡ ይህንን አዋጅ መሠረት በማድረግም የማዕድን ሚኒስቴር ለሚድሮክ ጐልድ እ.ኤ.አ. ጃንዋሪ 24 ቀን 2011 ክፍያዎች በአዲሱ አዋጅ መሠረት እንዲከናወኑ ማሳሰቡን ጠቅሰዋል፡፡

ይሁን እንጂ ቀደም ብሎ ለ20 ዓመታት የተገባን የውል ስምምነት አዲሱ አዋጅ ሊቀይር አይገባም በማለት፣ ሚድሮክ ጐልድ ከማዕድን ሚኒስቴር ጋር ለሦስት ዓመታት የተከራከረ መሆኑንና በመጨረሻም ሚኒስቴሩ በሚድሮክ ጐልድ አቋም መስማማቱን የሚገልጽ ደብዳቤ ጥር 28 ቀን 2005 ዓ.ም. መላኩን ገልጸዋል፡፡ በደብዳቤው መሠረትም ሚድሮክ ጐልድ በገባው ውል መሠረት እንዲቀጥል መደረጉን አስረድተዋል፡፡

ዋናው ኦዲተር ሪፖርቱን ለፓርላማ ከማቅረቡ በፊት ሙያው በሚጠይቀው መሠረት ከማዕድን ሚኒስቴር ወይም ከሚድሮክ ጐልድ ማግኘት የሚችለውን ሰነድ ሳይመረምር የሰጠው መግለጫ፣ በኩባንያው ላይ ተገቢ ያልሆነ ገጽታ እንዲያጠላበት በማድረጉ ማዘናቸውን ገልጸዋል፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ዋና ኦዲተር አቶ ገመቹ ዱቢሶ፣ ‹‹በሚድሮክ ጐልድ ላይ የኦዲት ቁጥጥር አናደርግም፡፡ ቁጥጥር ያደረግነው በማዕድን ሚኒስቴር ላይ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ይህ ቢሆንም በኦዲት መርህ መሠረት ተገቢው ምርመራ በሚኒስቴሩ ላይ መደረጉንና ለ20 ዓመታት የተደረገውን ውል መሠረት በማድረግ ተደርጐ የነበረውን ክርክርና የተሰጠውንም እልባት መመርመራቸውን ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ነገር ግን ፓርላማው ያወጣውን ሕግ ማዕድን ሚኒስቴር በደብዳቤ ሊቀይረው አይችልም፡፡ ፓርላማው ራሱ በአዋጁ ላይ ማሻሻያ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ኃላፊነት ደግሞ የመንግሥት ተቋማት ሕግን አክብረው መሥራታቸውን ተቆጣጥሮ ለፓርላማው መረጃ ማቅረብ ነው፤›› ብለዋል፡፡ በመሆኑም ማዕድን ሚኒስቴር በአዋጅ ቁጥር 678/2002 አንቀጽ 81 ላይ፣ ‹‹ይህ አዋጅ በሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት የተሰጠ ፈቃድ ወይም የተደረገ የማዕድን ስምምነት ከዚህ አዋጅ ጋር እስካልተቃረነ ድረስ ፀንቶ ለሚቆይበት ቀሪ ዘመን ተፈጻሚነቱ ይቀጥላል፤›› የሚለውን አንቀጽ ተላልፏል ብለዋል፡፡

በኦዲቱ ወቅት የሚድሮክን ጥያቄም ሆነ ሚኒስቴሩ የሰጠውን ምላሽ የኦዲት ቡድኑ ማየቱን የገለጹት ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ፣ ‹‹ተቀባይነት ያለው አሠራር አይደለም፤›› ብለዋል፡፡ በመሆኑም ማዕድን ሚኒስቴር ይህንንና ሌሎች በኦዲት የተለዩ የአሠራር ችግሮቹን ለማስተካከል የድርጊት መርሐ ግብር አውጥቶ ለዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት መላክ የሚኖርበት መሆኑንና መንግሥት ከሚድሮክ ጐልድ ያጣውን ገንዘብ ማስከፈል አለበት በማለት አስታውቀዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፓርላማው በ2006 ዓ.ም. በማዕድን አዋጁ ላይ ባደረገው ማሻሻያ፣ በኢትዮጵያ በከፍተኛ የማዕድን ልማት ብቸኛ የሆነውን ሚድሮክ ጐልድ የመከራከሪያ ነጥብ የተገነዘበ ማስተካከያ አድርጓል፡፡ 

የማሻሻያ አዋጁ 816/2006 በአንቀጽ 9 ‹‹ይህ አዋጅ በሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት የተሰጠ ወይም የተደረገ ማንኛውም የማዕድን ማምረት ፈቃድ ወይም የማዕድን ማምረት ስምምነት ፀንቶ ለሚቆይበት ቀሪ ዘመን፣ ፈቃዱ በተሰጠበት ወይም ስምምነቱ በተደረገበት ወቅት ተፈጻሚ በነበረው ሕግ መሠረት ባለበት ይቀጥላል፡፡ ሆኖም በፈቃዱ ወይም የስምምነቱ ዘመን አብቅቶ ሲታደስ በዚህ አዋጁ ድንጋጌዎች መሠረት ይፈጸማል፤›› የሚል ማስተካከያ አድርጓል፡፡ 

  

 

 

የአካባቢና የደን ሚኒስቴር ይፋ ያደረገው ጠቋሚ ዕቅድ የሙቀት አማቂ ወይም በካይ ጋዞች (ግሪን ሐውስ ጋዝ) ወደ ከባቢ አየር የሚለቀቁበትን መጠን በመቀነስ፣ በመጪዎቹ አምስት ዓመታት ውስጥ 147 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ላይ እንዲገደቡ ለማድረግ ማቀዱን አስታወቀ፡፡ 

 

ሚኒስቴሩ ባለፈው ሐሙስ ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ለውይይት ባቀረበው የአምስት ዓመት ሰነድ ላይ በአገሪቱ ለበካይ ጋዞች ወይም ለሙቀት አማቂ ጋዞች መለቀቅ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ዘርፎች ላይ የሚሠሩ ሥራዎች፣ የልቀት መጠኑን ለመቀነስ እንደሚያስችሉ አመላክቷል፡፡ የአካባቢና ደን ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኑርመደድ ጀማል ባቀረቡት የአምስት ዓመት መነሻ ዕቅድ መሠረት፣ በአገሪቱ ለሙቀት አማቂ ጋዞች ልቀት አስተዋጽኦ ከሚያደርጉት መካከል የደን መጨፍጨፍ፣ የአፈር መከላትና መሸርሸር፣ የጋማ ከብቶች ሲያመሰኩና እበት ሲጥሉ የሚመነጩ ጋዞች፣ የኢነርጂ ዘርፍና የመጓጓዣ ዘርፍ የሚያመነጩት፣ የኢንዱስትሪና የከተሞች መስፋፋት ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው፡፡ 

በመሆኑም እንስሳት ያመነጩታል ተብሎ የሚጠበቀውን የ88 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ልቀት ወደ 44 ሚሊዮን መቀነስ ከታቀዱት መካከል ይገኝበታል፡፡ በአፈር መከላትና መሸርሸር ምክንያት 40 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ጋዝ ይለቀቃል ተብሎ የሚጠበቅ በመሆኑ፣ ሚኒስቴሩ ይህንን መጠን ወደ 12 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ዝቅ የማድረግ ዕቅድ አስቀምጧል፡፡ 

መንግሥት ከአራት ዓመት በፊት በደቡብ አፍሪካ ይፋ ያደረገው የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የተነሳው ስትራቴጂ አካል የሆነው የመጪዎቹ አምስት ዓመታት ዕቅድ፣ በጠቅላላው በ147 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን የበካይ ጋዞችን ልቀት ለመቀነስ ተነስቷል፡፡ የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂው እንዳሰፈረው ከሆነ፣ እ.ኤ.አ. እስከ 2030 ባለው ጊዜ ውስጥ ሊመነጭ ይችላል ተብሎ የሚታሰበው ሙቀት አማቂ ጋዝ መጠን 400 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ነው፡፡ ሆኖም ካለፉት አምስት ዓመታት ጀምሮ በየዓመቱ እየመነጨ የሚገኘው በካይ ጋዝ መጠን 150 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን እንደሚገመት አስፍሯል፡፡ 

አቶ ኑርመደድ እንዳስታወቁት፣ በኢትዮጵያ የሚመነጨው የሙቀት አማቂ ጋዝ መጠን 0.3 በመቶ በመሆኑ ከዓለም አኳያ ያለው ድርሻ ዝቅተኛ ነው፡፡ ይህም ቢባል ግን የአገሪቱን የልቀት መጠን በታቀደው ዝቅተኛ መጠን ለማቆየትና በመጨረሻም ወደ ዜሮ ለማውረድ መንግሥት ያለፉት አምስት ዓመታትን ጨምሮ፣ በሃያ ዓመት ውስጥ 150 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው በአረንጓዴ ስትራቴጂው ማስፈሩ አይዘነጋም፡፡

 በሌላ በኩል መንግሥት ለመሠረተ ልማት ግንባታ ብቻ ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ 50 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልገው እንደነበር በአረንጓዴ ስትራቴጂ ሰነድ ላይ ያሰፈረ ሲሆን፣ በተጠናቀቀው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱም ጠቅላላ ዕቅዱን ለማስፈጸም ከ75 እስከ 79 ቢሊዮን ዶላር በጅቶ እንደነበርም አይዘነጋም፡፡ በተጠናቀቀው የአምስት ዓመት ዕቅድ ዘመን ውስጥ  ከዚህን ያህል ገንዘብ ውስጥ ምን ያህሉ እንደተገኘና ሥራ ላይ እንደዋለ መንግሥት ማብራሪያ እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡  

 

ለሁለት ቀናት በሸራተን አዲስ ሲካሄድ ቆይቶ የተጠናቀቀውን ጉባዔ በማስመልከት በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ተጨማሪ ፋይናንስ በማቅረብ ኢትዮጵያ የምትገነባቸውን ፕሮጀክቶች እንደምትደግፍ ቻይና ይፋ አደረገች፡፡ 

የቻይና ልማት ባንክ የዓለም አቀፍ ኦፕሬሽን ዘርፍ ምክትል ዳሬክተር ሺ ጂያንግ ከዓለም ባንክ ተጠሪ፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ፣ ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት (ዩኒዶ) ጋር በመሆን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት እንዳስታወቁት፣ ኢትዮጵያ ለምታካሂዳቸው የመሠረተ ልማትና የልማት ፕሮጀክቶች ባንካቸው ተጨማሪ ፈንድ ለመልቀቅ ዝግጁ ነው፡፡ 

በዚህም መሠረት ለኢንዱስትሪ ዞኖች ግንባታ፣ ለባቡር ትራንስፖርት፣ ለኤሌክትሪክ ኃይል ማሰራጫና ማስተላለፊያ የሚውል ፋይናንስ ለኢትዮጵያ እንደሚቀርብ ጂያንግ አስታውቀዋል፡፡ ጂያንግ ለጋዜጠኞች ሲያብራሩ፣ መንግሥታቸው በአፍሪካ ቅድሚያ ከሚሰጣቸው አገሮች መካከል ኢትዮጵያ ግንባር ቀደም በመሆኗ በተለይ ለኢንዱስትሪ ዞኖች ግንባታ የምታውለው ፋይናንስ ከቻይና ልማት ባንክ እንደሚቀርብ ገልጸዋል፡፡ 

ሊለቀቅ የሚችለው የገንዘብ መጠን ምን ያህል እንደሆነ ከመግለጽ የተቆጠቡት ጂያንግ፣ በተለይ በቅርቡ ፈንድ ሊያገኝ ይችላል ያሉት የኢንዱስትሪ ዞን የትኛው እንደሆነ መግለጽ አልፈለጉም፡፡ ሆኖም በድሬዳዋ የሚገነባው ኢንዱስትሪ ዞን ሊሆን እንደሚችል ፍንጮች ታይተዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በቅርቡ ይፋ የተደረጉ መረጃዎች እንደጠቆሙት፣ በሐዋሳ ለሚገነባው የኢንዱስትሪ ዞን የ250 ሚሊዮን ዶላር ፋይናንስ ከቻይና ተገኝቷል፡፡ በቦሌ ለሚ ለተገነባው የኢንዱስትሪ ዞን የዓለም ባንክ የ250 ሚሊዮን ዶላር ብድር መልቀቁ ይታወሳል፡፡ 

በርካታ የቻይና ኢንቨስተሮችና ባለሥልጣናት እንዲሁም ምሁራን የተሳተፉበት ጉባዔ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ ሲካሄድ፣ ‹‹ኢንቨስት ኢን አፍሪካ ፎረም›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶት ነው፡፡ በየዓመቱ በቋሚነት እንዲካሄድ ስምምነት መደረጉን፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አህመድ ሺዴ አስታውቀዋል፡፡

በሌላ በኩል ቻይና ለአፍሪካ የምትሰጠውን የልማት ፋይናንስ በዚህ ዓመት ወደ አምስት ቢሊዮን ዶላር ማሳደጓን አስታውቃለች፡፡ እስካሁን ለአፍሪካ አገሮች የልማት ድጋፍ በብድር ሲሰጥ የቆየው የገንዘብ መጠን ሦስት ቢሊዮን ዶላር የነበረ ሲሆን፣ በዚህ ዓመት መጨረሻ ወደ አምስት ቢሊዮን ማደጉን ጂያንግ ይፋ አድርገዋል፡፡ 

በአፍሪካ የቻይና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት እያደገ መምጣቱ ቢነገርም፣ ከዚህ ይልቅ ከፍተኛውን ድርሻ የያዘው የንግድ መጠን ነው፡፡ የቻይና ኩባንያዎች በአፍሪካ ኢንቨስት ያደረጉት መጠን ከአራት ቢሊዮን ዶላር እንደማይበልጥ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በአንፃሩ ለቻይና በሚያደላው የንግድ ልውውጥ ከ220 ቢሊዮን ዶላር በላይ ግብይት እንደሚፈጸም የቻይና ልማት ባንክ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ 

በኢትዮጵያ በቀጥታ ኢንቨስት ካደረጉ ኩባንያዎች መካከል ኋጂዬን ግሩፕ፣ ሐንሰም ኢንተርናሽናል ግላስ ኃላፊነቱ የተወሰነ ኩባንያ፣ እንዲሁም በቅርቡ ወደ አገር ውስጥ የገባው ጆርጅ ሹ ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች ለሙከራ ኢትዮጵያ የውጭ ኢንቨስትመንትን እንዴት ልታስተናግድ እንደምትችል ለመገምገም ሲባል የመጡ መሆናቸውን ጂያንግ ገልጸዋል፡፡ በእነዚህ ኩባንያዎች ኢንቨስትመንት ፈተናዎች አጋጥመዋል ያሉት ጂያንግ የጉምሩክ፣ የኃይል አቅርቦት፣ የውጭ ምንዛሪ እጥረት፣ የአስተዳደርና የሰው ኃይል፣ የገበያና የቴክኖሎጂ ችግሮች ማጋጠማቸውን አስታውቀዋል፡፡ 

አቶ አህመድ ሺዴ በበኩላቸው፣ አገሪቱ ለኢንዱስትሪ መስክ ጀማሪ በመሆኗ ያጋጠሙ ችግሮች እንዳሉ፣ በተለይ በኢንዱስትሪ ዞን ግንባታና አስተዳደር ላይ ከዜሮ በመነሳት ልምድ ለማካበት እየሞከረች መሆኗን ጠቅሰው፣ የቻይና ኢንቨስትሮች መምጣት መጀመራቸውንና ወደፊትም እየተበራከቱ እንደሚመጡ እምነታቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ 

 

የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ለ40 ዓመታት የራሱ ያደረገው ንብረት ለባለቤቶቹ እንዲመለስ ተወሰነ

በደርግ መንግሥት ከ13 ዓመታት በላይ ታስረው ኢሕአዴግ ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ ሲቆጣጠር በ1983 ዓ.ም. ከእስር የተፈቱት አምባሳደር ታደለች ኃይለ ሚካኤልና ቤተሰቦቻቸው፣ ለ40 ዓመታት በመንግሥት እጅ የነበረን

ንብረታቸውን በፍርድ ቤት ክርክር በመርታታቸው እንዲመለስላቸው ፍርድ ተሰጠ፡፡

በአዋጅ 47/67 ተወርሶ ንብረትነቱ ለመንግሥት እንደተዘዋወረ በመግለጽ፣ የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ በእነአምባሳደር ታደለች የቀረበበትን ክስ ያስተባበለ ቢሆንም፣ ያቀረባቸው ማስረጃዎች ፍርድ ቤቱን ሊያሳምኑ ባለመቻላቸው፣ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ፍትሐ ብሔር ችሎት፣ ንብረቱን ለከሳሾች እንዲያስረክብና በክስ ሒደቱ ወቅት ያወጡትን ወጪና ኪሳራ እንዲከፍል ፈርዶበታል፡፡ 

እነአምባሳደር ታደለች ከሁለት ዓመታት የፍርድ ቤት ክርክር በኋላ አሸናፊ ሆነው ፍርድ ያገኙበት የንብረት ክርክር የጀመረው፣ ደርግ የከተማ ቦታና ትርፍ ቤት አዋጅን ካወጀ ከ1967 ዓ.ም. ጀምሮ፣ በአባታቸው አቶ ዋኬኔ ፊሊጶስ (በኋላ ኃይለ ሚካኤል ፊሊጶስ ተብሏል) ነበር፡፡

የኅብረተሰባዊ ኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ መንግሥት በ1967 ዓ.ም. ባወጣው የከተማ ቦታና ትርፍ ቤት አዋጅ ቁጥር 47/67 መሠረት፣ ማንኛውም ትርፍ ቤት ያለው ነዋሪ አንዱን መርጦ እንዲወስድ ሲደረግ፣ አቶ ኃይለ ሚካኤል በአሁኑ አራዳ ክፍለ ከተማ ፒያሳ ወደ እሪ በከንቱ መውረጃና ወደ እቴጌ ጣይቱ ሆቴል መታጠፊያ አካባቢ የሚገኘውን ቤታቸውን (የአሁኑ ፓርክ ሆቴልን) ይመርጣሉ፡፡ በወቅቱ ቤቱ ኮሎኔል ሥዩም ኃይሌ የሚባሉ ባለሥልጣን ይኖሩበት ነበር፡፡ ቤቱ በባለሀብቱ የተመረጠ መሆኑ ተገልጾ ለኮሎኔል ሥዩም እንዲለቁ ደብዳቤ ይጻፍላቸዋል፡፡ አቶ ኃይለ ሚካኤል የመረጡት ቤት እስከሚለቀቅላቸው ድረስ፣ 160 ብር እየከፈሉ ተከራይተው ይኖሩበት የነበረው ቤት ኪራይ እንዲቆምም ተደርጓል፡፡ ኪራዩ እንዲቆም የተደረገው በሥራና ቤቶች ሚኒስቴር የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ነው፡፡ ቤቱን የያዙት ኮሎኔል ሥዩም ኃይሌ ግን ቤቱን ሊለቁ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ 

በሌላ በኩል ኮሎኔሉ ቤት አለቅም ቢሉም፣ አቶ ኃይለ ሚካኤል ለጊዜው የሚኖሩበት ቤት ለሌላ ሰው ሊሰጥ መሆኑ ተገልጾ ቤቱን ለቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ ይደርሳቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ከማስጠንቀቂያው ቀን በኋላ አቶ ኃይለ ሚካኤልን ከቤት አስወጥተው እንዳይጥሏቸው ሲባል በአስቸኳይ ቤት ተፈልጐ እንዲሰጣቸው፣ ለከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ኃላፊ ለነበሩት አቶ ኃይሌ ተድላ ደብዳቤ እንደተጻፈላቸው ለፍርድ ቤቱ በማስረጃነት የቀረቡ ሰነዶች ያስረዳሉ፡፡

ከላይ የተጻፉ ማስረጃዎች በእነአምባሳደር ታደለች በኩል የቀረቡ ሰነዶች መሆናቸውን ፍርድ ቤቱ በፍርዱ ገልጿል፡፡ ፍርድ ቤቱ በደረሰበት ድምዳሜ በ1969 ዓ.ም. እና በ1978 ዓ.ም. የተሰጡ የሰነድ ማስረጃዎች (በተለያዩ የመንግሥት አካላት) የሚያመለክቱት ቤቱ የአቶ ዋኬኔ (ኃይለ ሚካኤል) ፊሊጶስ መሆኑን እንደሆነ ገልጿል፡፡

አቶ ኃይለ ሚካኤል ሕይወታቸው እስካለፈበት 1972 ዓ.ም. ድረስ የመረጡትና እንዲረከቡ የተወሰነላቸውን ቤት ማግኘት አልቻሉም፡፡ እሳቸውን በመተካት ባለቤታቸው ወ/ሮ ብርአልጋ አንብሬ ክርክራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ነገር ግን በ1978 ዓ.ም. ደግሞ ቤቱ መኖሪያ ቤት ሳይሆን ድርጅት መሆኑ ተገልጾ፣ ጉዳዩ እስከሚጣራ በሚል ለአቶ ኃይለ ሚካኤል ቤተሰቦች አንድ ቤት ተመርጦ እንዲሰጣቸው ትዕዛዝ ተላለፈ፡፡ 

ተከሳሽ የሆነው የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ (ኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት) ቤቱ በአዋጅ ቁጥር 47/67 የተወረሰ መሆኑን የሚያስረዱለትን ማስረጃዎች ማቅረቡንም ፍርዱ ይገልጻል፡፡ በወቅቱ ቤቱ እንዲመለስላቸው ለከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር አቤቱታ አቅርበው፣ በ1982 ዓ.ም. መመለስ እንደማይቻልና ማካካሻ ግምት እንዲሰጣቸው መወሰኑን የሚያሳይ ሰነድ ለፍርድ ቤቱ ማቅረቡንም አስረድተዋል፡፡

ኤጀንሲው ያቀረበው ሰነድ ግን አቶ ኃይለ ሚካኤል ወይም ቤተሰቦቻቸው ያቀረቡት ሰነድ ሳይሆን፣ ቤቱን አለቅ ብለው አሻፈረኝ ያሉት የኮሎኔል ሥዩም መሆኑን እንደሚያስረዳ ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡

ቤቶች ኤጀንሲ ቤቱ በአዋጅ ቁጥር 47/67 የተወረሰ መሆኑን የኢትዮጵያ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ሥራ አመራር ቦርድ ማረጋገጡን ገልጾ ሰነድ ያቀረበ ቢሆንም፣ ሰነዱ የሚያስረዳው ግን ስለቤቱ የተነሳው ጉዳይ ለኤጀንሲው ከተሰጠው ሥልጣን ውጪ መሆኑን ጠቅሶ መዝገቡን እንደዘጋው መሆኑን ፍርድ ቤቱ ጠቅሷል፡፡

አዋጅ ቁጥር 47/67 አንቀጽ 16(1) የሚደነግገው፣ በአንድ ከተማ ውስጥ ከአንድ መኖሪያ ቤት ውጪ ትርፍ ቤት ያለው ሰው፣ በራሱ ፍላጐት አንድ መኖሪያ ቤት በመምረጥ መልሶ መረከብ እንደሚችል ነው፡፡ የንግድ ቤት ወይም ከአንድ ቤተሰብ በላይ የሚያስተናግድ መሆኑ በከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር የተረጋገጠ ከሆነ፣ የማይመለስና ማካካሻ የሚሰጥ እንደሆነ ፍርድ ቤቱ ጠቅሷል፡፡

በመሆኑም ቤቶች ኤጀንሲ ቤቱ የንግድ እንደሆነና ከሳሾች ማካካሻ እንዲወስዱ የተከራከረ ቢሆንም፣ ማስረጃ አለማቅረቡን ገልጿል፡፡ በአዋጅ ቁጥር 47/67ም ቤቱን እንደመረጡና ለአቶ ኃይለ ሚካኤል እንደተወሰነላቸው እንጂ፣ ንግድ ቤት ስለመሆኑ ምንም ያለው እንደሌለ አስረድቷል፡፡ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲም ማረጋገጡን አክሏል፡፡ ፍርድ ቤቱ በአጠቃላይ ከሳሾች ካቀረቡት የሰነድ ማስረጃ አኳያ ከሳሾች ቤቱን በውርስ ያገኙት ስለመሆኑ መገንዘቡን አውስቷል፡፡

የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 14ኛ ፍትሐ ብሔር ችሎት ሰኔ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. የአቶ ኃይለ ሚካኤል ፊሊጶስ ወራሾች፣ አምባሳደር ታደለች ኃይለ ሚካኤልና አቶ ዓለማየሁ ኃይለ ሚካኤል ንብረቱ ይገባቸዋል የሚል ፍርድ የሰጠው ባደረገው የሰነዶች ምርመራ ነው፡፡ 

ክሱ በ2005 ዓ.ም. ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍትሐ ብሔር ችሎት ቀርቦ ተከሳሽ የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ፣ ቤቱ በአዋጅ ቁጥር 47/67 የተወረሰ መሆኑንና ከሳሾች ወራሾች ባልሆኑበት የመንግሥት ንብረት መከራከር እንደማይችሉ ገልጾ ያቀረበውን መከራከሪያ ሰምቶ፣ ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም. ክሱን ውድቅ አድርጐት ነበር፡፡ በክሱ ላይ ግን ከሳሾች አሁን ፍርድ እንዲያገኙ ያደረጓቸው ሰነዶችን አያይዘው አቅርበው ነበር፡፡

እነአምባሳደር ታደለች ግን ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ በማለታቸው፣ ፍርድ ቤቱ ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ብይን ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ብይን እንደገለጸው፣ ከሳሾች ያቀረቧቸው ሰነዶች ቤቱ በአቶ ዋኬኔ (ኃይለ ሚካኤል) ፊሊጶስ ስም ነው፡፡ በመሆኑም ወራሾች የአቶ ዋኬኔ ፊሊጶስ ወራሾች ናቸው፡፡ በመሆኑም ክሱ ውድቅ የሚሆን ባለመሆኑና ብይኑ ግድፈት ያለበት መሆኑን በመጥቀስ፣ የሥር ፍርድ ቤት ወደ ፍሬ ነገሩ በመግባት ሁለቱን ወገኖች አከራክሮ ተገቢውን ውሳኔ እንዲሰጥ በማዘዝ መዝገቡን መመለሱን ሰነዶች ያስረዳሉ፡፡ ክሱ የተመለሰለት የሥር ፍርድ ቤት (አሁን ፍርድ የሰጠው ፍርድ ቤት) አምስት ጭብጦችን ይዟል፡፡ ከሳሾች ባለቤት መሆን አለመሆናቸውን፣ ቤቱ በአዋጅ ቁጥር 47/67 መወረስ አለመወረሱን፣ ካልተወረሰ ተከሳሽ ለከሳሾች ቤቱን ማስረከብ አለበት የለበትም፣ በኤጀንሲውና ቤቱን በተከራየው ሁለተኛ ተከሳሽ አሁን ቤቱን ፓርክ ሆቴል ብሎ እየሠራበት ያለውና ከኤጀንሲው የተከራየው ነጋዴ መካከል ያለው የኪራይ ውል ካልፈረሰ፣ ቤቱን ለከሳሾች ማስረከብ አለበት የለበትምና ወራሾች የቤቱ ባለቤት ስለመሆናቸው የግድ በአዋጅ ቁጥር 47/67 መሠረት ማስረዳት አለባቸው የለባቸውም የሚሉ ጭብጦችን በመያዝ፣ ከላይ የተዘረዘሩትን ምርመራዎች በማድረግ ፍርድ መስጠቱን ሰነዶቹ ያብራራሉ፡፡ ኤጀንሲው ቤቱን እንዲያስረክብ፣ የወጪና ኪሳራም ተሰልቶ ሲቀርብ እንዲከፍል ተፈርዶበታል፡፡     

 

በኢትዮጵያ ስላለው የመብት ረገጣ 90 ሚሊዮን ህዝብ ምስክር ነው” – ለእድገታችን አሜriካ ምስክር ሆነችልን ማለት ውጤት አያመጣም – ዶ/ር መረራ በአለማቀፍ ታላላቅ የሚዲያ አውታሮች መነጋገሪያ ሆኖ የዘለቀው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ኢትዮጵያን የመጐብኘት ውጥን አሜሪካ አምባገነን መንግስታትን ከመደገፍ የመነጨ በመሆኑ እምብዛም ትኩረት የሚሠጠው ጉዳይ አይደለም ብለዋል – የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፡፡ ዶ/ር መራራ ጉዲና በአዲስ አበባ […]

ሰበር ዜና ================================================ ትናንት ሀሙስ ዕለት ሰኔ 25 2007 ዓ.ም የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ሰራዊት በትግራይ ክልል ቀፍታ መሲል፣ ሆርጃሞ እና ማይሰገል ላይ ህወሓት ከሚቆጣጠረው የ24ኛ ክፍለ ጦር፣ ፌደራል ፖሊስና ልዩ ኃይል ጋር ባደረገው ለአራት ሰዓታት የዘለቀ ከባድ ጦርት ከፍተኛ ጉዳት አደረሰ፡፡ የአርበኞች ግንቦት 7 አርበኛ ተጋዮች በትግራይ ቀፍታ መሲልና ሆርጃሞ ላይ መሽጎ […]

በህወሓት መከላከያ ሰራዊት ውስጥ ተፈጥሮ የቆየው መከፋፈል በሁለት ፅንፍ የቆመ ሲሆን አንደኛው ቡድን በኤታማጆር ሹሙ ጀነራል ሳሞራ የኑስ ስር ሁለተኛው ቡድን ደግሞ የምስራቅ ዕዝ አዛዥ ከነበረው ሌ/ጀነራል አብርሃ ወ/ማርያም ጎን የተሰለፉ ናቸው፡፡ ሌ/ጀነራል አብርሃ ወ/ማርምን ከዕዝ አዛዥነቱ አንስቶ ወደ መከላከያ መምሪያ የማዛወሩ የእነ ጀነራል ሳሞራ የኑስ ቡድን ዕቅድ በሌ/ጀነራል አብርሃ ቡድን የበላይነት ሊከሽፍ ችሏል፡፡ ሆኖም […]

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስራ ‹‹ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ በማወክ›› የተከሰሰችው ሜሮን አለማየሁ የ6 ወር እስር ተፈረደባት፡፡ ሜሮን አለማየሁ ሚያዝያ 14 በተጠራው ሰልፍ ላይ ‹‹ወያኔ ሌባ፣ መንግስት የለም፣ አትነሳም ወይ፣ የታረደው ወገን ያነተ አይደለም ወይ›› በሚል ሁከትና ብጥብጥ ፈጥራለች ተብላ በተከሰሰችበት በዋስ ወጥታ ጉዳዩን ስትከታተል የቆየች ሲሆን ዛሬ […]

ዜጎች በፖለቲካ አመለካከታቸው ከቀያቸው እየተፈናቀሉ ነው በምስራቅ ጎጃም ዞን አርሶ አደሮች ‹‹የማዳበሪያ ዕዳ አልከፈላችሁም›› በሚል በገፍ እየታሰሩ መሆኑን ምንጮች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ አርሶ አደሮቹ ከ1989 ዓ.ም ጀምሮ ወስዳችኋል የተባሉትን የማዳበሪያ እዳ እንዲከፍሉ እየተጠየቁ እንደሆነ የገለጹት ምንጮች በአንድ ቀበሌ ብቻ በመቶዎች የሚቆጠሩ አርሶ አደሮች በጅምላ መታሰራቸውን ገልጸዋል፡፡ አርሶ አደሮች እነሱ ወስደውታል የተባለውን ብቻ ሳይሆን በሞት የተለዩትን […]

ሰበር ዜና፡- ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሔር የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ሆነው ተሾሙ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሊቀ መንበር ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሔር፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ሆነው ተሾሙ፡፡

ዶ/ር አዲሱ የምርጫ ቦርድ ምክትል ሊቀ መንበር በመሆን ያለፉትን ሁለት አጠቃላይ ምርጫዎች ያገለገሉ ሲሆን፣ ገዢው ፓርቲና አጋሮቹ 547ቱንም የፓርላማ መቀመጫ ያሸነፉበትን የ2007 ዓ.ም አጠቃላይ ምርጫ በመምራት በሕግ የተፈቀደላቸውን የሥልጣን ዘመን አጠናቀዋል፡፡ 

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ የዶ/ር አዲሱን፣ የምክትል ኮሚሽነርና የኮሚሽን አባላት ሹመት በሙሉ ድምፅ አፅድቆታል፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ሆነው ላለፉት አምስት ዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩት አምባሳደር ጥሩነህ ዜና በዶ/ር አዲሱ ተተክተዋል፡፡

   

በመወያኔ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ አለመግባባቱ ተባብሶ መቀጠሉ ታወቀ በታላቁ አንዋር መሰጂድ ከባድ ተቃውሞ ተደረገ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የኢትዮጵያ ጉብኝት በዓለም ዙርያ ቁጣ ቀስቅሷል።  አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ  ዘመቻ ተጀመረ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በአቶ አንዳርጋቸው አያያዝ ዙሪያ ማስጠንቀቂያ መስጠታቸው ተሰማ በመወያኔ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ አለመግባባቱ ተባብሶ መቀጠሉ ታወቀ በመከላከያ ሰራዊት የሰሜን እዝ አባላት የሆኑት ወታደሮች በአገልግሎት ማብቂያ በሚል […]

By Redeat Bayleyegn የ32ኛው የኢትዮጵያ ስፖርት ፌዴሬሽን በሰሜን አሜሪካ አመታዊ ቶርናመንት ደረሰ። ከጁን 28 እስከ ጅላይ 4 2015 በዩኒቨርስቲ ኦፍ ሜሪላንድ በርድ ስቴድየም ይካሄዳል። 31 ቡድኖች ከ25 የሰሜን አሜሪካ ከተሞች ለውድድሩ ይመጣሉ ፥ ካልጋሪና ቶሮንቶ ካናዳን ጨምሮ። በቀላሉ መገመት እንደሚቻለው …

የኳስ ንግሥና የኢትዮጵያውያን አመታዊ በአል Read more »

ዛሬ ሰኔ 26 ቀን 2007 ዓ.ም ልደታ ፍርድ ቤት 11ኛ ችሎት ቀርበው በቂሊንጦ ታስሮ ሚገኘው ማስተዋል ፈቃዱ ባለመቅረቡ የአቃቢ ህግ ይግባኝ ሳይታይ ቀርቶአል፡፡ ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬ እና ቤተለሄም አካለወርቅ ትናንት በዛቻ እና ማስፈራራት ክስ ቄራ ምድብ ችሎት ቀርበው በዋስ እንዲወጡ ቢታዘዝም ካሳንቺዝ ስድስተኛ ፖሊስ ግን ታሳሪዎቹን ለመልቀቅ ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል፡፡ ጠዋት በልደታ […]

በርካታ ድርጅቶች በግል ጡረታ አዋጅ ማሻሻያ ላይ ያላቸውን ቅሬታ ለፓርላማ አቀረቡ

በርካታ የግል ድርጅቶችና የሲቪክ ማኅበራት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅን ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ያላቸውን ቅሬታ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቀረቡ፡፡ የምክር ቤቱ የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ማሻሻያውን አስመልክቶ

ባዘጋጀው የሕዝብ አስተያየት መስጫ መድረክ ላይ የተጋበዙ ከ300 በላይ የሚሆኑ የግል ድርጅቶችና ሲቪክ ማኅበራት፣ ማሻሻያውን ያረቀቀው የግል ድርጅት ሠራተኞች ማኅበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ ባለድርሻ አካላትን ሳያነጋግር ወይም ሳያወያይ ይህንን ረቂቅ ማሻሻያ ለፓርላማ ማቅረቡ ፍፁም ተገቢ አይደለም ሲሉ ወቅሰዋል፡፡ 

በዋናነት ከተካተቱት ማሻሻያዎች መካከል በግል ድርጅት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁጥር 715/2003 ቀደም ሲል የፕሮቪደንት ፈንድ ሥርዓት በፈቃደኝነት እንዲቀጥል ቢወሰንም፣ በማሻሻያው ግን ወደ ግል ሠራተኞች ጡረታ ፈንድ ይዞራል የሚለው ይገኝበታል፡፡ 

ይህ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ከቀረበ በኋላ ግን አርቃቂው አካል የግል ድርጅት ሠራተኞች ማኅበራዊ ኤጀንሲ ማሻሻያውን በድጋሚ በማየት ፕሮቪደንት ፈንዱ በቀጥታ ይዞራል ወይም የተጠራቀመው ገንዘብ ወደ ጡረታ ፈንድ ይገባል የሚለው እንዲስተካከል ማድረጉን የኤጀንሲው የሥራ ኃላፊዎች በውይይቱ መጀመርያ ላይ ተናግረዋል፡፡ 

በውይይቱ እንዲገኙ የተጋበዙት ድርጅቶች በሙሉ ሠራተኞቻቸውን በፕሮቪደንት ፈንድ ዋስትና የሚያስተዳድሩ በመሆናቸው፣ በመጀመርያ እፎይታቸውን ገልጸዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል የሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር አረጋ ይርዳው ይገኙበታል፡፡ 

‹‹ይህንን ማሻሻያ በመስማቴ ደስ ብሎኛል፤›› ያሉት ዶ/ር አረጋ መንግሥት ስለ ግል ሠራተኞች ማኅበራዊ ዋስትና ማሰብ ከመጀመሩ በርካታ ዓመታት ቀደም ብሎ፣ የግል አሠሪዎችና ሠራተኞቻቸው ተነጋግረው ፕሮቪደንት ፈንድ ሥርዓትን መፍጠራቸውን አስታውሰዋል፡፡ 

‹‹ስለዚህ ፕሮቪደንት ፈንድ የአሠሪና የሠራተኛው የግላቸው ነው፡፡ ማንም ሌላ ሰው ሊወስንበት አይችልም፤›› ብለዋል፡፡ በዚህም መልክ መወሰኑን ጥሩ ነው ብለዋል፡፡

ሲአርዲኤ የተባለው የሲቪክ ማኅበራት ጥላ ዋና ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት ዶ/ር መሸሻ ሸዋረጋ፣ በተመሳሳይ የማሻሻያ አዋጁ አርቃቂዎች ባለድርሻ አካላትን አወያይተናል በማለት ያቀረቡት ሪፖርት ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡ 

በሲአርዲኤ ሥር ከ350 በላይ ሲቪክ ማኅበራት የሚገኙ መሆኑንና ኢትዮጵያ ከዚህ ዘርፍ በዓመት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደምታገኝ አስታውሰው፣ ይህንን ዘርፍ እንደ ባለድርሻ አካል ሳያወያዩ ሪፖርት ማድረግ ተገቢ አለመሆኑን ጠቁመዋል፡፡ 

የአዋጁ አርቃቂዎች ባለድርሻ አካላትን አወያይተናል የሚሉት የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማኅበራት ኮንፌዴሬሽንና የአሠሪዎች ፌዴሬሽን ነው፡፡ 

‹‹ዛሬ በድፍረት መናገር ያለብኝ ይመስለኛል፡፡ እነዚህ ተቋማት እንደማይወክሉን ታውቃላችሁ፡፡ እንዲያውም ለመንግሥት ነው የሚሠሩት፤›› ሲሉ ዶ/ር አረጋ ይርዳው ተችተዋል፡፡ 

ዶ/ር መሸሻ ፕሮቪደንት ፈንድን በቀጥታ ወደ ጡረታ እንዳይዞር በመጨረሻ መወሰኑን ተቀብለዋል፡፡ ‹‹ይሁን እንጂ ፕሮቪደንት ፈንድ ምንም እንዳልሠራ መቆጠር የለበትም፡፡ በ2003 ዓ.ም. እንደተፈቀደው ሁሉ አሁንም በሠራተኞች ምርጫ ሊቀጥል ይገባል፤›› ብለዋል፡፡ 

የሲቪክ ማኅበራት ፀባይ ከሌሎቹ ስለሚለይ ሠራተኞች የሚቆዩት ፕሮጀክቶች እስካሉ ድረስ ብቻ ስለሆነ፣ ፕሮጀክቶች ሲያበቁ እንደሚሰናበቱ አስታውሰዋል፡፡ 

ዶ/ር መሸሻ ሠራተኞች በሚሰናበቱበት ጊዜ ለሥራ መፈለጊያም ሆነ ቤተሰቦቻቸውን ማስተዳደሪያ ሆኖ የሚያገለግለው ፕሮቪደንት ፈንድ በመሆኑ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል፡፡ ምክንያቱም እንደ ሌላው አገር ኢትዮጵያ ውስጥ እንደ ‹ኢምፕሎይመንት ፈንድ› ወይም ሥራ አጥ በሚኮንበት ወቅት የኑሮ ዋስትና አለመኖሩን ጠቅሰዋል፡፡ ‹‹እኛ አገር ይህ ባለመኖሩ ፕሮቪደንት ፈንድን ይዞ መቀጠል ምን ችግር አለው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ 

የሴንተር ፎር ዲስኤቢሊቲስ ዴቨሎፕመንት ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ የትነበርሽ ንጉሤ በበኩላቸው፣ ‹‹የፕሮቪደንት ፈንድ ሊቀጥል ይገባል፡፡ ምክንያቱም በተለይ ወጣት ሥራ ፈጣሪዎችን የሚያበረታታ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ወጣቶች እስከ 60 ዓመት ዕድሜያቸው በተቀጣሪነት ቆይተው የጡረታ ተከፋይ እንዲሆኑ የሚያደርግ ነው ብለዋል፡፡ 

የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤትን ወክለው የተገኙት የሕግ ባለሙያው አቶ ዮሐንስ ወልደ ገብርኤል፣ ‹‹የፕሮቪደንት ፈንድ ማኅበራዊ ዋስትና ሥርዓት የራሱ ደካማ ጎኖች አሉት፡፡ እነዚህ ደካማ ጎኖች ግን መንግሥት ለፕሮቪደንት ፈንድ ጥበቃ ለመስጠት ኃላፊነት ባለመውሰዱ የተከሰቱ ችግሮች እንጂ የግሉ ዘርፍ የፈጠረው አይደለም፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ፕሮቪደንት ፈንድ ለግሉ ዘርፍ ትልቅ ዋስትና ነው፡፡ አሠሪው ለሠራተኛው ዋስትና እንዲኖረው የሚያደርግ ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) ምክትል ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፣ ኮንፌዴሬሽኑ ከኤጀንሲው ጋር በተወያየበት ወቅት ፕሮቪደንት ፈንድን በተመለከተ ኮንፌዴሬሽኑ ያቀረበው ሐሳብ የጡረታ ዐቅድ እየሰፋ በሄደ ቁጥር ፕሮቪደንት ፈንድ እየተዋጠ እንደሚሄድ፣ በመሆኑም በራሱ ጊዜ ሊሞት ስለሚችል መነካካት አያስፈልግም የሚል እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ 

አሁንም ቢሆን ፕሮቪደንት ፈንድን የማይፈልጉ ድርጅቶች ብቻ ወደ ጡረታ በምርጫቸው እንዲመጡ መደረግ እንዳለበት ኢሠማኮ እንደሚያምን ተናግረዋል፡፡ ሌሎች በውይይቱ ላይ የተሳተፉ ግለሰቦችም ፓርላማው ይህንን አዋጅ በዚህ ዓመት ሊያፀድቀው እንደማይገባ ተከራክረዋል፡፡ 

ይህንን ያሉበት ምክንያት የረቂቅ አዋጁ አንቀጽ 19 ላይ የተደረገው ማሻሻያን በመቃወም ነው፡፡ አንቀጹ ‹‹በተቀጠረ ሦስት ዓመት ወይም ከዚህ ባነሰ ጊዜ ውስጥ በጡረታ የሚገለል ሠራተኛ፣ በጡረታ ከሚገለልበት ወር ሦስት ዓመት አስቀድሞ ባለው ወር ሲከፈለው ከነበረው መደበኛ የወር ደመወዝ በ25 በመቶ የሚበልጥ ዓመታዊ አማካይ የደመወዝ ጭማሪ ያገኘ እንደሆነ፣ በየዓመቱ 25 በመቶ ያለው የደመወዝ ጭማሪ ብቻ በደመወዙ ላይ ተደምሮ የሦስት ዓመት አማካይ የወር ደመወዙ ተይዞ ይታሰባል፤›› ይላል፡፡ 

ይህንን የተቃወሙት የድርጅት ተወካዮቹ አገሩን በዝቅተኛ ደመወዝ ሲያገለግሉ የነበሩ የመንግሥት ሠራተኞችን፣ ወታደሮችንና የመሳሰሉትን የሚጎዳ ነው ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ በዕድሜው መጨረሻ ላይ የተሻለ ገንዘብ ቢያገኝ ለአገሩ ያበረከተውን በገንዘብ የማይለካ አስተዋጽኦ ወደጎን በመተው፣ 25 በመቶ ጭማሪውን ብቻ ማሰብ ተገቢ አይደለም በማለት ተቃውመዋል፡፡ 

የኤጀንሲው የሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ግርማ ሲሳይ ፕሮቪደንት ፈንድን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፣ ፕሮቪደንት ፈንድ ዘለቄታዊ ማኅበራዊ ዋስትና መሆን አይችልም ብለዋል፡፡ 

‹‹የፕሮቪደንት ፈንድ ገንዘብን የወሰደ ሠራተኛ ገንዘቡ ካለቀበት አለቀበት ነው፡፡ በማኅበራዊ ዋስትና (በግል ጡረታ) ቢታቀፍ ግን አሥር ዓመት ብቻ አገልግሎ ዕድሜ ልኩን እስከነ ተተኪዎቹ ሚስቱንም ጨምሮ ዕድሜው ስልሳ ዓመት ከደረሰ በኋላ ማግኘት ይችላል፤›› ብለዋል፡፡ 

አንቀጽ 19 ላይ የተደረገውን ማሻሻያ በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፣ አንድ ሠራተኛ በመንግሥት መሥሪያ ቤት ውስጥ ከ25 ዓመት በላይ ያገለግልና በ25/55 የጡረታ መብት መሠረት በአምስት ሺሕ ብር ጡረታውን አስከብሮ፣ ቀሪውን ዕድሜ ማለትም አምስት ዓመቱን በግል ድርጅት በወር እስከ 30 ሺሕ ብር ቢቀጠር አጠቃላይ የጡረታ አበሉ የሚሰላው በ30 ሺሕ ብር ደመወዝ ተመን ነው፡፡ ያላዋጣውን በመብላት ፈንዱን የሚያደርቀው በመሆኑ ገደብ ሊጣልበት የሚገባ ነው ብለዋል፡፡ 

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ፀጋዬ ገብረ ሚካኤል በበኩላቸው፣ ማኅበራዊ ዋስትናን በተመለከተ በየትም አገር ስምምነት ኖሮ እንደማያውቅ ገልጸዋል፡፡ በኋላ ላይ የኅብረተሰቡን ዋስትና ማስከበር የመንግሥት ኃላፊነት በመሆኑ ኃላፊነቱን እንደሚወጣ ተናግረዋል፡፡ 

የፓርላማው የማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወ/ሮ አበባ ዮሴፍ፣ ከውይይቱ በርካታ ቁም ነገሮችን መገኘታቸውን፣ ለፓርላማ የቀረበ ነገር ሁሉ እንደማይፀድቅ፣ በተደረገው ውይይት ላይ በድጋሚ በመነጋገር ተጨማሪ የሕዝብ ውይይት ካስፈለገም ሊጠራ እንደሚችል አስረድተዋል፡፡ 

 

አዳዲስ የፋይናንስ ድጋፎች በሚጠበቁበት ፎረም የቻይና ባለሥልጣናትና ኩባንያዎች ታድመዋል

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ጨምሮ የቻይናና የኢትዮጵያ መንግሥታት የፋይናንስና የኢኮኖሚ ሚኒስትሮች፣ የዓለም ባንክና የሌሎች ዓለም አቀፍ ተቋማት ኃላፊዎችና ኢንቨስተሮች የተገኙበት ፎረም፣ ቻይና በአፍሪካ

ስለምታካሂደው የኢንቨስትመንትና የንግድ ልውውጥ እየመከረ ነው፡፡ አዳዲስ ስምምነቶችና የፋይናንስ ድጋፎች ይፋ እንደሚደረጉበት ይጠበቃል፡፡ 

‹‹ኢንቨስቲንግ ኢን አፍሪካ ፎረም›› በሚል ስያሜ የመጀመሪያውን ጉባዔ በኢትዮጵያ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም እንዳስታወቁት፣ በአፍሪካ ከ2,200 ያላነሱ ኩባንያዎች በተለያዩ መስኮች ኢንቨስት አድርገዋል፡፡ በኢትዮጵያም ኋጂዬን ግሩፕ የተባለው ጫማ አምራች 3,500 ሠራተኞችን በመቅጠር፣ በዓመት ሁለት ሚሊዮን ጫማዎችን በማምረት ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ 

ከካቻምና ጀምሮ በኢትዮጵያ ኢንቨስት ካደረጉ የውጭ ኩባንያዎች የሚገኘው የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት 1.2 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የቱርኩ አይካ አዲስን ጨምሮ የታይዋኑ ጆርጅ ሹ ኩባንያና ሌሎችም ሥራዎችን እያስፋፉ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ አዳዲሶቹ ፒቪኤችና ኤችኤንድኤም የተባሉ ትልልቅ ኩባንዎች ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውም፣ በዓመት 13 በመቶ እያደገ ለሚገኘው አምራች ኢንዱስትሪው ትልቅ ተስፋ እንደሆነ አቶ ኃይለ ማርያም ተናግረዋል፡፡ 

የቻይና ምክትል የፋይናንስ ሚኒስትሯ ሊዩ ዢያንሁዋ፣ እንዲሁም የቻይና ልማት ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ዩዋን ሊ ባደረጉት ንግግር፣ አገራቸው ከአፍሪካ ጋር ያላትን የንግድና የኢንቨስትመንት ትስስር ለማጠናከር እንደምትፈልግ አስታውቀዋል፡፡ በተለይ ዩዋን ሊ እንዳሉት፣ ባንካቸው በ34 የአፍሪካ አገሮች ውስጥ በቻይና-አፍሪካ ልማት ፈንድ በኩል እ.ኤ.አ. በ2006 በ82 ፕሮጀክቶች ላይ ኢንቨስት ካደረገው የ3.15 ቢሊዮን ዶላር ገንዘብ በተጨማሪ፣ 16 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስት የማድረግ ሐሳብ አለው፡፡ ይህም ወደ አፍሪካ የሚመጣውን የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ፣ የአፍሪካን የወጪ ንግድ በየዓመቱ በሁለት ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ፣ እንዲሁም የታክስ ገቢንም በአንድ ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡ በአንፃሩ እስካሁን በቻይና ኩባንያዎች አፍሪካ ውስጥ በውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት አማካይነት የተመዘገበው አራት ቢሊዮን ዶላር መሆኑን የገለጹት ምክትል ፕሬዚዳንት ሊ፣ የሁለትዮሽ ንግዱ ግን 222 ቢሊዮን ዶላር ማስመዝገቡን ጠቅሰዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ አብዛኛው ከቻይና ወደ አፍሪካ የሚገቡ ሸቀጦች የሚሸፍኑት መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ 

በኢትዮጵያ ቻይናውያን ያስመዘገቡት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በሚመለከት የዓለም ባንክ ካቻምና አካሂዶት በነበረው ጥናት መሠረት፣ እ.ኤ.አ. ከ2004 እስከ 2011 ባለው ጊዜ ውስጥ ከቻይና ወደ ኢትዮጵያ የሚመጣው ኢንቨስትመንት በየዓመቱ በአማካይ የ58 ሚሊዮን ዶላር ጭማሪ አሳይቷል፡፡ ይህም ቢባል ግን የቻይና ኩባንያዎች በመንግሥት የታክስና ጉምሩክ አስተዳደር የሚታዩ ውጣ ውረዶች፣ በውጭ ምንዛሪ በኩል መንግሥት ግልጽነት አለማሳየቱን፣ በሠራተኛ ሕግ፣ በሠለጠነ የሰው ኃይል አቅርቦትና በመሳሰሉት መስኮች ላይ ችግሮች እያጋጠሟቸው እንደሚገኙ የዓለም ባንክ በጥናቱ አሳይቷል፡፡ 

በሰው ጉልበት ዋጋ መወደድና በማምረቻ ወጪዎች ከፍተኛነት ሳቢያ ከቻይና እየነቀሉ ወደ አፍሪካ የሚመጡ የቻይና ኩባያዎች እንደሚበራከቱ ከሰባት ዓመት በፊት ጀምሮ ሲነገር ነበር፡፡ በዚህ መስክ ኢትዮጵያ መጠቀም አለባት በማለት ደጋግመው ሲናገሩ እንደነበር የሚታወሱት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ናቸው፡፡ ሆኖም የተገመተውን ያህል ግን በርካታ የቻይና ኩባንያዎች ሳይመጡ ቀርተዋል፡፡ ይህንን በሚመለከት ሪፖርተር ያነጋገራቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ልዩ ረዳት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ አገሪቱ ይህንን ዕድል ለመጠቀም በሚያስችላት ደረጃ ዝግጁ እንዳልነበረች ገልጸዋል፡፡ ይህም ሆኖ በአሁኑ ወቅት በኢንዱስትሪ ፓርኮች አማካይነት የመሠረተ ልማት ጥያቄዎችንና ሌሎች እንደ ጉምሩክ ሥነ ሥርዓት ያሉ አገልግሎቶችን በፋብሪካዎቻቸው ደጅ ማግኘት የሚችሉበት ሥርዓት መዘርጋቱን ጠቅሰዋል፡፡ 

በአፍሪካ ኢንቨስት ስለማድረግ በዝግ እየመከረ የሚገኘው ጉባዔም መሠረታዊ በሚባሉ ችግሮች ላይ ከመነጋገር ባሻገር፣ በአፍሪካ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በመገንባት ረገድ አዳዲስ ስምምነቶች ላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በሌሎችም የመሠረተ ልማት መስኮች ላይ የቻይና መንግሥት ኢትዮጵያን ጨምሮ ለአፍሪካ አገሮች የሚደረጉ አዳዲስ ብድሮችንና የፋይናንስ ድጋፎችን ይፋ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ 

በአፍሪካ የዓለም ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ማክታር ዲዮፕ እንዳስታወቁት፣ በአፍሪካ በየዓመቱ የ90 ቢሊዮን ዶላር የመሠረተ ልማት ግንባታ ፍላጎት ቢኖርም፣ የአፍሪካ አገሮች ኢንቨስት ማድረግ የቻሉት ግን ከ20 ቢሊዮን ዶላር ያልዘለለ ነው፡፡ ይህንን በመንተራስ የቻይና ኩባንያዎች በቋሚ ንብረቶች ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እንዳላቸው፣ የቻይና የፋይናንስ ተቋማትም አስፈላጊውን ፋይናንስ ለማቅረብ ፍላጎት እንዳላቸው ታውቋል፡፡ 

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴርን ጨምሮ የዓለም ባንክ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት (ዩኒዶ) እንዲሁም የቻይና መንግሥት ያዘጋጁት ይህ ፎረም፣ በየዓመቱ በአፍሪካና በቻይና እየተፈራረቀ በቋሚነት እንዲካሄድ ስምምነት መደረጉን የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አህመድ ሺዴ አስታውቀዋል፡፡ 

 

 

  

 

ኤጀንሲው 31 ሺሕ ያህሉ ከፍለው መዋዋላቸውን አስታውቋል

-የተዋዋሉት ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ከፍለዋል

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለአሥረኛ ጊዜ ባወጣው የኮንዶሚኒየም ቤት ዕጣ ዕድለኛ ከሆኑ የከተማው ነዋሪዎች መካከል አራት ሺሕ ተመዝጋቢዎች ለክፍያ ይጠበቃሉ፡፡

ክፍያቸውን በሁለት ሳምንት ውስጥ ካላጠናቀቁ ቤቶቹን እንደማያገኙ ተገለጸ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቤቶች ልማት አስተዳደር ኤጀንሲ ዕጣ ከወጣላቸው 35 ሺሕ ዕድለኞች ውስጥ 31 ሺሕ ያህሉ ውል መፈጸማቸውን አስታውቋል፡፡

ዕጣው ከደረሳቸው መካከል 31 ሺሕ ያህሉ ውል ተዋውለው መጨረሳቸውንና ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ቅድመ ክፍያ መፈጸሙን አስታውቋል፡፡ ቀሪዎቹ ዕድለኞችም እስከ ሐምሌ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ ውላቸውን ፈጽመው መጨረስ እንዳለባቸው አሳስቧል፡፡ ውል የመፈጸሚያ ጊዜው ካለፋቸው ቤቱን እንደማያገኙም አስታውቋል፡፡ 

መክፈል ያልቻሉ ዕጣው የወጣላቸው ዕድለኞች ደግሞ ቅድመ ክፍያ (ሃያ በመቶውን) ለመክፈል ከፍተኛ ችግር ውስጥ መግባታቸውን ይናገራሉ፡፡ ብዙዎቹ በብድርና በተለያዩ ወገኖች ድጋፍ ሊከፍሉ መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ ከአቅማቸው በላይ የሆነ ኪራይ እየከፈሉ መሆኑን የሚናገሩት ነዋሪዎቹ፣ ለደረሳቸው ኮንዶሚኒየምና ለሚኖሩበት የቤት ኪራይ በየወሩ መክፈል ስለማይችሉ፣ ክፍያውን በሁለት ሳምንት አጠናቁ በመባላቸው ከወዲሁ ሥጋት ገብቷቸዋል፡፡ 

አራት ኪሎ፣ ልደታና ለመሀል ከተማው ቀርበው በተሠሩ ኮንዶሚንየም ቤቶች የደረሳቸው ዕድለኞች፣ ኮንዶሚኒየም ቤቱ ባይፀዳ እንኳን ገብተው ለኪራይ የሚከፍሉትን እየከፈሉ እንደሚኖሩ የገለጹት ዕድለኞቹ፣ ከመሀል ከተማው በ10 እና በ15 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የደረሳቸው ግን ግራ እንደተጋቡ ተናግረዋል፡፡ 

ቤቶቹ የተገነቡት አገር ውስጥ በተመረቱ የግንባታ ግብዓቶች በመሆኑ ቅናሽ እንዲደረግላቸው የሚጠይቁት ነዋሪዎቹ፣ የመሠረተ ልማት ባልተሟላባቸው አካባቢዎች ዕጣ የደረሳቸው በኮንዶሚኒየም ቤቶቹ አካባቢ ትምህርት ቤቶች እስከሚከፈቱና ትራንስፖርት ተሟልቶ እስከሚገባ ድረስ፣ የባንክ ክፍያ መጀመሪያው ጊዜ እንዲያራዝምላቸው ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ያለፉና በመሰናዶ ትምህርት ቤት የተመደቡ ልጆቻቸውን እንዴት አጓጉዘው ማስተማር እንደሚችሉ ሥጋት ውስጥ እንደከተታቸው ተናግረዋል፡፡ 

በሌላ በኩል ዕጣ የወጣላቸው የተወሰኑ ዕድለኞች ቅድሚያ ክፍያ የሚከፍሉት አጥተው በየመሥሪያ ቤቱ፣ በካፌ፣ በሬስቶራንትና በመዝናኛ ቦታዎች በመገኘት እውነቱን እየተናገሩ ዕርዳታ እየጠየቁ መሆኑ ታውቋል፡፡ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አንዳንዶቹ ዕድለኞች ከአሥር ዓመታት ቆይታ በኋላ የደረሳቸው ዕድል መሆኑን ገልጸው፣ ይህ ዕድል ካመለጣቸው ዳግመኛ ስለማያገኙት ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸውን ዕርዳታ በመጠየቅ ለማሟላት እየተሯሯጡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በልመና ምን ያህሉን መሸፈን እንደሚችሉ አለማወቃቸውን የሚናገሩት ዕድለኞቹ፣ እስከ መጨረሻው ቀን ድረስ የቻሉትን ጥረት አድርገው ካልሞላላቸው ምንም ማድረግ ስለማይችሉ ሳይወዱ በግድ እንደሚተውት ተናግረዋል፡፡

የቤቶች ልማት አስተዳደር ኤጀንሲ ግን ቤቶቹን ለማዋዋል የተቀመጠው ቀነ ገደብ ሐምሌ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. ስለሚያበቃ፣ በአስቸኳይ መዋዋሉን እንዲያጠናቅቁ አስታውቋል፡፡ የዕጣ ዕድለኞች የሆኑት አራት ሺሕ ያህል ግለሰቦች በተቀመጠው ቀነ ገደብ ውስጥ የማያጠናቅቁ ከሆነ ቤቶቹን እንደማያገኙ ገልጿል፡፡ 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ በተለይ በአሥረኛው ዙር ዕጣ የወጣባቸው ኮንዶሚኒየም ቤቶች ዋጋ በመጋነኑ ምክንያት፣ ልዩ ኮሚቴ አቋቁሞ የዋጋውን ሁኔታ ማጥናት መጀመሩ የታወቀ ቢሆንም፣ አሁን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ለማወቅ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡   

 

ከአዲስ አበባ እስከ ጂቡቲ ወደብ ድረስ የተዘረጋው የባቡር መስመር ጥቅምት 2008 ዓ.ም. ሥራ የሚጀምር ቢሆንም፣ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበረክት የሚችለውን ነዳጅ ለማጓጓዝ፣ የሚያስፈልገው የመሠረተ ልማት ቀደም ብሎ አለመጠናቀቁ አለመግባባት ፈጠረ፡፡ 

ኢትዮጵያ የምትጠቀመው አብዛኛው ነዳጅ የሚገባው በጂቡቲ በኩል ሲሆን የሚጫነውም ከሆራይዘን ተርሚናል ነው፡፡ ነገር ግን የተገነባው የባቡር መስመር ቀጥታ ወደ ጂቡቲ ወደብ የሚያመራ ነው፡፡ የአገሪቱ ነዳጅ ወደሚጫንበት ሆራይዘን ተርሚናል የባቡር ሐዲድ አለመገንባቱ አለመግባባት መፍጠሩን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ 

ከሆራይዘን ተርሚናል ባቡሩ ነዳጅ ቢጭን እንኳን የተጫነው ነዳጅ ኢትዮጵያ ከደረሰ በኋላ የሚያራግፍበት ዲፖ አለመገንባቱ ሌላ ችግር እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ ጉዳዩ ላይ የበለጠ አለመግባባት የፈጠረው የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን፣ የትራንስፖርትና የዕቃ ማጓጓዣ ባቡሮችን እንዲያመርት ከቻይናው ኩባንያ ኖሪንኮ ጋር አስቀድሞ ውል መግባቱ ነው፡፡ ኖሪንኮ በበኩሉ ከአገር በቀሉ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር በገባው ውል መሠረት ከ50 በላይ የሚሆኑ የነዳጅ ማመላለሻ ባቡር ፉርጎዎች ተመርተው ለሥራ ዝግጁ መሆናቸውን እየገለጸ ነው፡፡ 

የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ኃይለ ማርያም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የእሳቸው ኩባንያ ከውጭ ነዳጅ ገዝቶ ጂቡቲ ሆራይዘን ተርሚናል ያራግፋል፡፡ ከዚህ በኋላ የነዳጅ ኩባንያዎች በተሽከርካሪዎች ለአገር ውስጥ ገበያ ያቀርባሉ፡፡ ነገር ግን ነዳጅን በባቡር ለማጓጓዝ ወደ ሆራይዘን ተርሚናል የሚጓዝ የባቡር ሐዲድ አልተገነባም፡፡ በአገር ውስጥም ማጠራቀሚያ ዲፖ አልተገነባም፡፡ ‹‹ጉዳዩ በደንብ መታየት ነበረበት፡፡ ትንሽ ክፍተት አለው፤›› በማለት አቶ ታደሰ የጉዳዩን አሳሳቢነት ገልጸዋል፡፡ 

ይህ ጉዳይ ክፍተት እንዳለው ዘግይቶ የተገነዘበው ትራንስፖርት ሚኒስቴር አጀንዳ ቀርጾ መሠረተ ልማት ለማሟላት ውይይት ማካሄድ መጀመሩ ታውቋል፡፡ 

ትራንስፖርት ሚኒስቴር፣ በሥሩ የሚገኘውን ትራንስፖርት ባለሥልጣን፣ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝንና አሥሩን ነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች በማሰባሰብ በመፍትሔ ሐሳቦች ላይ እየተነጋገረ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

በዋናነት የቀረበው መፍትሔ ከጂቡቲ ወደብ ወደ ሆራይዘን ተርሚናል የሚወስድ የባቡር ሐዲድ መዘርጋትና በሆራይዘን ተርሚናል ባቡሮቹ ነዳጅ የሚጭኑባቸውን መሣሪያዎች ማሟላት ነው፡፡

በአገር ውስጥ ደግሞ አዲስ አበባ (ሰበታ) አካባቢ በሚገኘው ግዙፍ የባቡር ተርሚናል ውስጥ የነዳጅ ማራገፊያ ዲፖ መገንባት ዋነኛ ጉዳይ ሆኗል፡፡ በአሁኑ ወቅት እነዚህ ጉዳዮች በውይይት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ ግንባታዎቹን ለማካሄድ የበጀት ጉዳይ ቀጣዩ መነጋገሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡ 

ምንጮች እንደገለጹት፣ በጀት ተወስኖ የግንባታ ቦታ ከተዘጋጀ ግንባታው ከሁለት እስከ ሦስት ዓመት የሚፈጅ በመሆኑ፣ በባቡር መሠረተ ልማት ነዳጅ ለማመላለስ ረዥም ጊዜ ሊወስድ ይችላል፡፡ ይህ ፕሮግራም ቀድሞ ባለመታሰቡ ብቻ የተገነባው የባቡር መሠረተ ልማት ላልተወሰነ ጊዜ ነዳጅ ከማመላለስ ውጪ ይሆናል፡፡

በጂቡቲ ሆራይዘን ተርሚናል ነዳጅ በተሽከርካሪ የሚያቀርቡ ኩባንያዎች አሥር ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ በወር በ250 ሚሊዮን ዶላር ወጪ በሚያቀርበው ነዳጅ ትልቅ ድርሻ ያላቸው ኖክ፣ ቶታል፣ ኦይል ሊቢያና የተባበሩት ናቸው፡፡ እነዚህና ሌሎች ስድስት ኩባንያዎች በመላው አገሪቱ ባላቸው ከ250 በላይ ነዳጅ ማደያዎች አማካይነት ነዳጅ ሲያቀርቡ ቆይተዋል፡፡ 

ሰበታ አካባቢ የነዳጅ ዲፖ እንደሚገነባ የሚጠበቀው በግል ኩባንያዎቹ ሲሆን፣ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከጂቡቲ ነዳጅ እያጓጓዙ በዲፖው የማራገፍ ኃላፊነት እንዳለበት ይጠበቃል፡፡ ኩባንያዎቹ ደግሞ በተሽከርካሪዎች ወደ ነዳጅ ማደያዎች ያደርሳሉ በሚለው ዕቅድ ላይ ውይይት እየተካሄደ መሆኑም ታውቋል፡፡ 

ከአዲስ አበባ (ሰበታ) እስከ ጂቡቲ ወደብ ድረስ የተዘረጋው የባቡር መስመር 656 ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው፡፡ መስመሩ እስከ አዳማ ድረስ ሁለት ባቡሮች በአንዴ የሚያስተናግድ ሲሆን፣ ከአዳማ እስከ ጂቡቲ ድረስ ደግሞ አንድ መስመር ይኖረዋል፡፡

የባቡር መስመሩ ለመንገደኞችና ለዕቃ አገልግሎት የሚሰጥ በመሆኑ የትራንስፖርት ወጪን በ50 በመቶ ይቀንሳል ተብሏል፡፡ በሁለት የቻይና ኩባንያዎች እየተገነባ ያለው ይህ የባቡር መስመር የሐዲድ ማንጠፍ ሥራው የተጠናቀቀ በመሆኑ፣ በመጪው ጥቅምት አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ተብሏል፡፡ ነዳጅ ለማጓጓዝ በተፈጠረው ክፍተት ላይ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ጌታቸው በኩረ አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡  

 

ከ123 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣበት የአፍሪካ የሰላም ማዕከል በአዲስ አበባ ተገነባ

ለአፍሪካ ሰላምና ደኅንነት እንቅስቃሴዎች ድጋፍ እንዲሰጥ ታስቦ በአዲስ አበባ የተገነባውና ከ123 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣበት የሰላም ማዕከል፣ ሰኔ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመርቆ ተከፈተ፡፡ 

ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ መርቀው የከፈቱት ይኼ የደኅንነት ተቋም፣ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በመላው አፍሪካ ግጭትን ለመፍታት ለሚደረጉ የሰላም ማስከበር ጥረቶች አስፈላጊ የሥልጠናና የጥናት ማዕከል ሆኖ እንዲያገለግል ታስቦ የተገነባ ነው፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት፣ የተሳካ ሰላም የማስከበር ሥራዎች ለማከናወን ማዕከሉ ትልቁ አስተዋጽኦ ያበረክታል፡፡ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ማዕከሉን አስመልክተው ሲናገሩ፣ ‹‹የሰላም ማዕከሉ ወታደራዊና የሰላም አስከባሪ ተቋማት ዓላማቸውን በተሳካ ሁኔታ እንዲወጡ የምርምርና የሥልጠና አገልግሎት በመስጠት የሰላም ማስከበር ሥራዎች ማዕከል ሆኖ ያገለግላል፤›› ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያና ከኢትዮጵያ ውጪ ሰላምና ደኅንነት ከማስጠበቅ አንፃር ላደረገው አስተዋጽኦ አድናቆታቸውን ለመከላከያ ሚኒስቴር የቸሩት ፕሬዚዳንት ሙላቱ፣ የአገሪቱ መረጋጋትና የኢኮኖሚ ዕድገት ምክንያት ኢትዮጵያ በአካባቢው የሰላምና የፀጥታ ተምሳሌት መሆን በመቻሏ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ 

የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ በበኩላቸው፣ በዓለም አቀፍ ደረጃም ኢትዮጵያ ሰላምን በማስከበር ሥራዎች የማይተካ ሚና እየተጫወተች እንደምትገኝ ገልጸው፣ ማዕከሉ ይህንን ጥረት በዕውቀትና በምርምር ለመደገፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡

በአዲስ አበባ የተገነባው ይኼው የሰላም ማዕከል ግጭትን ለመከላከል፣ ዕርቅ ለመፍጠርና ሰላም ለማስከበር ለአካባቢውና ለመላው አፍሪካ ጥቅም ይውል ዘንድ፣ በተለይ ከአፍሪካ ኅብረትና ከምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) ጋር በትብብር እንደሚሠራ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማጆር ሹም ጄኔራል ሳሞራ ዩኑስን ጨምሮ፣ በርካታ የመከላከያና የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡    

 

የአይኤስ አሸባሪ ቡድን ሊቢያ ውስጥ በኢትዮጵያውያን ላይ በፈጸመው አሰቃቂ ግድያ ምክንያት መንግሥት በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ረብሻ በመፍጠር ተከሰው የተፈረደባቸው የሰማያዊ ፓርቲ አባላት፣

የእስር ጊዜያቸውን ጨርሰው ሲወጡ ከማረሚያ ቤት በራፍ ላይ ተይዘው ከተመሠረተባቸው ክስ በዋስ እንዲለቀቁ ብይን ተሰጠ፡፡

የፓርቲው አባላት ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. እያንዳንዳቸው በ5,000 ብር ዋስ እንዲለቀቁ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቄራ ምድብ ችሎት ብይን የሰጠው በወይንሸት ሞላ፣ በኤርሚያስ ፀጋዬ፣ በዳንኤል ተስፋዬና በቤተልሔም አካለ ወርቅ ላይ ነው፡፡

በተከሳሾቹ ላይ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ተሰጥቶ የነበረው፣ ሰላማዊ ሠልፉን በማወክ የተለያዩ ስድቦችን መንግሥትንና ዜጎችን በመሳደብ፣ ሥርዓቱን በማንጓጠጥና በፖሊስ አባላት ላይ ድንጋይ በመወርወር ወንጀል ተከሰው ነው፡፡

ፍርደኞቹ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፍርድ በቀረቡበት ዕለት ሁለት ወር ከአንድ ቀን በእስር መቆየታቸው በመረጋገጡ፣ በዕለቱ ከእስር እንዲፈቱ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ የሰጠ ቢሆንም ፖሊስ ሌላ ወንጀል መፈጸማቸውን በመግለጽ፣ ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ከእስር ተፈትተው ወደ ቤታቸው ለማምራት ማረሚያ ቤት ደጃፍ ላይ ሲደርሱ ተይዘው ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል፡፡

ፖሊስ ለፍርድ ቤት ያቀረበው ክስ፣ ተከሳሾቹ ቀደም ብሎ በተከሰሱበት ወንጀል ላይ በምስክርነት ያቀረባቸውን ማስፈራራታቸውንና መዛታቸውን በመግለጽ ነው፡፡ ፍርድ ቤቱ ክሱን ተቀብሎ ለሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. መዛታቸውን የሚያስረዱለትን ምስክሮቹን እንዲያቀርብ ቀጠሮ የሰጠ ቢሆንም፣ ፖሊስ ምስክሮቹን በተለያዩ ምክንያቶች ሊያቀርብ አለመቻሉን ገልጾ፣ ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ጠይቋል፡፡ 

ተከሳሾቹ ግን ፖሊስ ምስክሮቹን በተሰጠው ቀጠሮ ቀን ማቅረብ እንደነበረበት ገልጸው፣ ፍርድ ቤቱ ዋስትና እንዲፈቅድላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ጥያቄውን ተቀብሎ እያንዳንዳቸው በ5,000 ብር ዋስ እንዲለቀቁ ፈቅዷል፡፡ በሌላ በኩል ተከሳሾቹ ቀደም ብሎ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ሁለት ወራት ተፈርዶባቸው በነበረውና እስራቸውን ጨርሰው በወጡበት ክስ፣ ዓቃቤ ሕግ ይግባኝ እንዳለባቸውና ሰኔ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ ተጠቁሟል፡፡

 

አፍሪካ ከእስያ አገሮች ትልቅ ፉክክር ይጠብቃታል  

የአሜሪካና የአፍሪካ የእርስ በርስ የኢኮኖሚ ግንኙነት ላይ ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ታምኖበት ላለፉት 15 ዓመታት ሲተገበር የቆየውን ከታሪፍና ከኮታ ነፃ የገበያ ዕድል፣ ለተጨማሪ አሥር ዓመታት ማራዘሙን የአሜሪካ ኮንግረስ ይፋ አደረገ፡፡ 

ከታሪፍና ከኮታ ነፃ የገበያ ዕድል ወይም ‹‹አፍሪካ ግሮውዝ ኤንድ ኦፖርቹኒቲ አክት – አጎዋ›› ሚያዝያ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በአምባሳደር ማይክል ፍሮማንና አምባሳደር ሱዛን ራይስ በኩል ቀርቦለት ሲመክር የከረመው ሕግ መወሰኛው ምክር ቤት፣ ለመጪዎቹ አሥር ዓመታት እንዲራዘም ይፋ ያደረገው አጎዋ እንደከዚህ በፊቱ ሳይሆን በእስያ አገሮች ዘንድ ፈተና እንደሚገጥመው እየተነገረለት ነው፡፡ አምባሳደር ፍሮማን የአሜሪካ የንግድ ዘርፍ ተወካይ ሲሆኑ፣ የቀድሞዋ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር አምባሳደር ሱዛን ራይስ በአሁኑ ወቅት የአሜሪካ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ናቸው፡፡ በአምባሳደሮቹ የቀረበው የአጎዋ ረቂቅ ሕግ ለአሥር ዓመታት የሚራዘም ከሆነ ከ30 በላይ ለሚሆኑ የአፍሪካ አገሮች ትልቅ እፎይታ ይሆናል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በኮንግሬሱ ተቀባይነት አግኝቶ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በፊርማቸው እንዲያፀድቁት መርቶታል፡፡ 

እ.ኤ.አ. በ2009 ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በጋና ተገኝተው አሜሪካ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ትስስር የማጠናከር አስፈላጊነት ሲገልጹ፣ ‹‹ለልጆቻችን ማውረስ የምንፈልገውን ዓለም በመቅረፅ ረገድ አፍሪካ የአሜሪካ አጋር ነች፡፡ አጋርነታችንም በጋራ ኃላፊነትና በመከባበር ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል፤›› ብለው ነበር፡፡ ባለፈው ዓመት የአፍሪካና የአሜሪካ የመሪዎች ጉባዔ በተካሄደበት ወቅት፣ ፕሬዚዳንቱ የአፍሪካ የዕድገትና የገበያ ዕድል የሚያበቃበት ጊዜ ማለትም የመጪው ዓመት መስከረም ወር ደርሶ ከመጠናቀቁ በፊት፣ የጊዜ ገደቡ እንዲራዘም ኮንግረሱን መጠየቃቸውም ይታወሳል፡፡ በዚህ መሠረት አጎዋ እንዲራዘም መጠየቅ ብቻ ሳይሆን፣ ማሻሻያዎች ተደርገውበት የበለጠ ውጤታማ የሚሆንበት መንገድ እንዲመቻች ሲጠየቅ እንደቆየ አይዘነጋም፡፡

ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገትና የገበያ ዕድል ለመፍጠር በሚል መነሻ እ.ኤ.አ. በ2000 ሕግ ሆኖ የፀደቀው አጎዋ፣ በአሜሪካና በአፍሪካ መካከል እያደገ ስለመምጣቱ ለሚነገርለት አጋርነት መጠናከር አስተዋጽኦ ማድረጉን በማስረጃ ደፍገው የሚያቀርቡት የአሜሪካ ባለሥልጣናት ብቻ አይደሉም፡፡ አፍሪካውያንም ይጠቀሳሉ፡፡ በአፍሪካ ወሳኝ የልማትና የዕድገት መርሐ ግብሮች እንዲከናወኑ፣ የተለያዩ የአኅጉሪቱ ቀጣናዎች የኢኮኖሚ ጥምረት እንዲፈጥሩ፣ ኩባንያዎች ተወዳዳሪ እንዲሆኑና የግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ ለሚያደርገው የካፒታልና የኢንቨስትመንት ፍሰት ምቹነትን በመፍጠር በኩል ሚናው አሌ እንደማይባል የሚገልጹ አሉ፡፡  

በአልባሳት ንግድ ዘርፍ ከተሰማሩ ተቋማት በተገኘ መረጃ መሠረት ከነዳጅ መስክ ውጭ ያለው የወጪ ንግድ፣ መርሐ ግብሩ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ በቀጥታ ወደ 350,000 ለሚቆጠሩ ሰዎች የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር፣ በተዘዋዋሪም ሌሎች በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩትን በማገዝ ዘርፉን በሦስት እጥፍ አሳድጎታል፡፡ 

የአፍሪካን ልማት ከመደገፍ ባሻገር አጎዋ ለአሜሪካ ተጨባጭ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎችንም አስገኝቷል፡፡ እ.ኤ.አ. ከ2000 ጀምሮ አሜሪካ ከሰሃራ በታች ወዳሉት አገሮች የምትልካቸው ሸቀጦች መጠን ይበልጥ እየጨመረ መምጣቱን የሚያመላክቱ ክስተቶች በአፍሪካ እየታዩ ነው፡፡ መካከለኛ ገቢ ያለው የኅብረተሰብ ክፍል እያደገ መጥቶ ከሩብ ቢሊዮን በላይ እንደሚደርስ የኢኮኖሚ ትንበያዎች ይጠቁማሉ፡፡ በመሆኑም በአሜሪካ የተመረቱ ሸቀጦችን የመሸመት አቅማቸው በማደጉ፣ የሸቀጦች ወጪ ንግድ መጠን በሦስት እጥፍ ሊጨምር ችሏል፡፡ በአፍሪካ የሚገኙ የንግድ ተቋማት የአሜሪካ ግብዓቶች፣ ዕውቀት፣ ክህሎትና አጋርነት አስፈልጓቸዋል፡፡ አሜሪካ በአፍሪካ የምታደርገው የኢንቨስትመንት ፍሰት፣ በአፍሪካም ሆነ በአሜሪካ ለሚገኙ ሠራተኞች የሥራ ዕድሎችን ከመፍጠሩም በላይ፣ ገቢያቸው እንዲያድግ ምክንያት ሆኗል፡፡ 

አሜሪካ በአጎዋ በኩል ከአፍሪካ ጋር የምታደርገውን የንግድ ልውውጥ እንዳፋጠነ የሚነገርለት ቢሆንም፣ አብዛኞቹ የአፍሪካ አገሮች ግን ተጠቃሚ ሳይሆኑበት እንደቀረ ይታወቃል፡፡ በግብርና ውጤቶች፣ በጨርቃ ጨርቅና አልባሳት፣ በቆዳና የቆዳ ውጤቶች አኳያ ተጠቃሚ መሆን ከሚገባቸው አገሮች አንዷ ኢትዮጵያ እንደነበረች ይታመናል፡፡ ቢሆንም በአጎዋ በኩል አገሪቱ ከቀረጥና ከኮታ ነፃ ወደ አሜሪካ የላከቻቸው ምርቶች መጠን እጅግ ዝቅተኛ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ 

ኢትዮጵያ ባለፉት አሥራ አምስት ዓመታት ውስጥ በአጎዋ በኩል ከላከቻቸው ምርቶች በአማካይ በዓመት ከ40 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማግኘት አልቻለችም፡፡ ከሪፖርተር ጋር ቆይታ ያደረጉት የአሜሪካ ከፍተኛ የንግድ ባለሙያና በኢትዮጵያ የአሜሪካ የውጭ ንግድ አገልግሎት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ታንያ ኮል እንዳስታወቁት፣ አሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ በአጎዋ በኩል ከምትልካቸው ምርቶች ቦይንግ አውሮፕላንን ጨምሮ በዚህ ዓመት ብቻ ከ1.6 ቢሊዮን ዶላር በላይ ስታገኝ፣ ኢትዮጵያ ግን ከ225.6 ሚሊዮን ዶላር የዘለለ ገቢ አላገኘችም፡፡ በመሆኑም ምርቶችን በገፍ ማምረትም ሆነ ወደ አሜሪካ መላክ ፈተና ሆኖ ይገኛል፡፡ ለሚቀጥሉት አሥር ዓመታት አጎዋ በመራዘሙ ግን እየተስፋፉ ያሉት የቆዳና የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ትልቅ የገበያ ዕድል እንደሚያገኙ ይጠበቃል፡፡ በአንፃሩ አሜሪካ ከታሪፍና ከኮታ ነፃ የገበያ ዕድል ለእስያ አገሮች ‹‹ትራንስ ፓስፊክ ፓርትነርሺፕ›› በተሰኘው ማዕቀፍ ውስጥ ተመሳሳይ የነፃ ገበያ ዕድል መስጠቷ ግን በርካታ ጨርቃ ጨርቅ አምራቾችን ሥጋት ውስጥ የጣለና የአፍሪካን የተወዳዳሪነት አቅም የሚፈታተን ተብሎለታል፡፡ የሥጋቱ ምክንያት ደግሞ በእስያ አገሮች ውስጥ የማምረቻ ወጪዎች ከአፍሪካ ይልቅ ዝቅተኛ መሆናቸው ነው፡፡ 

 

የዶ/ር አርከበ ዕቁባይ አዲስ መጽሐፍ ለኢትዮጵያ ገበያ ቀረበ

ዋጋው በጣም ውድ ነው ተብሏል

ዶ/ር አርከበ ዕቁባይ ‹‹ሜድ ኢን አፍሪካ ኢንዱስትሪያል ፖሊሲ ኢን ኢትዮጵያ›› በሚል ርዕስ ያሳተሙት አዲስ መጽሐፍ፣ በኢትዮጵያ ገበያ ቀረበ፡፡

መጽሐፉ በዓለም ገበያ ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀረበ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በቡክ ወርልድ አማካይነት ገበያውን ተቀላቅሏል፡፡

ዋቢና ኢንዴክስን ጨምሮ 348 ገጽ ያለው ይህ የዶ/ር አርከበ ዕቁባይ መጽሐፍ፣ ከአፍሪካ አጠቃላይ ሁኔታ በመነሳት የኢትዮጵያን ኢንዱስትሪ በጥልቀት ይተነትናል፡፡

ዶ/ር አርከበ ለዚህ መጽሐፍ መነሻ የሆናቸው በለንደን ስኩል ኦፍ ኦርየንታል ኤንድ አፍሪካን ስተዲስ ለተከታተሉት የዶክትሬት ዲግሪ ማሟያ ያቀረቡት ጽሑፍ ነው፡፡

ዶ/ር አርከበ በአራት ዓመት የሚጠናቀቀውን ትምህርታቸውን በዩኒቨርሲቲው ባልተለመደ ሁኔታ በ23 ወራት ውስጥ በከፍተኛ ማዕረግ በማጠናቀቃቸው፣ በወቅቱ ከፍተኛ አድናቆትን ተችሯቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡

የተመረቁበትን ዴቨሎፕመንት ስተዲስ የዶክትሬት ዲግሪ የጥናት ጽሑፍ በማስፋት በመጽሐፍ መልክ ያዘጋጁት ሲሆን፣ የተማሩበት ለንደን ስኩል ኦፍ ኦርየንታል ስተዲስ ይኼንን መጽሐፍ እንዲታተም ለኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ልኮታል፡፡

ለዶ/ር አርከበ ቅርበት ያላቸው የሪፖርተር ምንጮች እንደገለጹት፣ ዶ/ር አርከበ ይኼንን መጽሐፍ ያዘጋጁት በዘርፉ ጥልቅ ጥናት አካሂደው ነው፡፡

ዶ/ር አርከበ መጽሐፉን ለማዘጋጀት በ150 ኩባንያዎች ላይ ጥልቅ ጥናት ማድረጋቸው፣ ሃምሳ ፋብሪካዎችን በአካል በመገኘት ማጥናታቸው፣ ለዚሁ ጽሑፍ 250 ጥያቄዎችን በማዘጋጀት ከፋብሪካዎች መረጃ እንደሰበሰቡና ከሁለት እስከ አራት ሰዓት የፈጁ 200 ቃለ መጠይቆችን ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡ ለኢንዱስትሪ ልማት ማነቆ ናቸው የተባሉ ችግሮችን ለመለየት በውጭና በአገር ውስጥ የሚገኙ ፋብሪካዎች ላይ ጥናት ማድረጋቸው እንዲሁ ተነግሯል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች ጥናቶች መረጃ ሆነው ያልቀረቡ አንድ ሺሕ ሰነዶችን በማገላበጥ የተሟላ ጥናት ማድረጋቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ይህ አጠቃላይ ጥናት አራት ዓመት የፈጀ መሆኑም ተገልጿል፡፡

ይህ የዶ/ር አርከበ መጽሐፍ የተወሳሰቡ የኢንዱስትሪ ፖሊሲ ሐሳቦችን በጥልቅ አረዳድ የተነተነ ነው ሲሉ አስተያየት ሰጪዎች ገልጸዋል፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው ‹‹ጸሐፊው በንድፈ ሐሳብ ብቻ ሳይሆን በተግባራዊ ልምዳቸውና በፖሊሲ ቀረፃ የረዥም ጊዜ ልምድ ስላላቸው ነው፤›› በማለት የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ሀ ጁን ቻንግ ለመጽሐፉ ያላቸውን አድናቆት በመጽሐፉ ላይ ገልጸዋል፡፡ 

የቀድሞ የዓለም ባንክ ዋና ኢኮኖሚስት ጀስቲን ይፋ ሊን በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በልማት ተዓምር እየፈጠረች በመሆኑ ለአፍሪካ አገሮች መነቃቃት፣ በራስ መተማመንና መልካም ተሞክሮ ማካፈል ትችላለች ያሉ ሲሆን፣ ዶ/ር አርከበ ይኼን ለውጥ በመጽሐፉ በግሩም ሁኔታ እንደተረኩት መስክረዋል፡፡ ጃፓን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ለምሥራቅ እስያ አገሮች ምሳሌ እንደሆነችው ሁሉ፣ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አገሮች ተመሳሳይ አስተዋጽኦ ማበርከት ትችላለች ብለዋል፡፡ መጽሐፉ ኢትዮጵያ ዕድገቷን እንዴት እያፋጠነችና ባለሁለት አኃዝ ዕድገት እያስመዘገበች እንደመጣች፣ ጥልቅ ግንዛቤ ይሰጣል በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ 

መጽሐፉ በእንግሊዝ ገበያ ውስጥ 55 ፓውንድ ሲሸጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ደግሞ 1,815 ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል፡፡

ከቡክ ወርልድ የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው፣ የመጽሐፉ ዋጋ መወደዱን ከተለያዩ አቅጣጫዎች አስተያየት እየተሰጠበት ነው፡፡ መጽሐፉ ሊወደድ የቻለው ሐርድ ከቨር ያለውና ደረጃውን ጠብቆ በመታተሙ፣ እንዲሁም በጣም የተለፋበት በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡

መጽሐፉ በዋነኛነት ትኩረት የሚያደርገው በኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት መሄድ ባለባቸው አቅጣጫዎች ላይ ነው፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍን ማሳደግ ለግብርና የላቀ ዕድገት ወሳኝ መሆኑም ተተንትኗል፡፡

ዶ/ር አርከበ በመጽሐፉ መግቢያ ላይ እንደጠቀሱት፣ በመጽሐፉ ያንፀባረቋቸው ምልከታዎች የመንግሥትንም ሆነ አብረዋቸው እየሠሩባቸው ወይም የሠሩባቸው ተቋማትን አይወክሉም፡፡ የመጽሐፉ ዋናው ዓላማ የተለያዩ ምልከታዎች፣ ልምዶችና ተግዳሮቶችን ለማቅረብ ለተጨማሪ ጥናትና ውይይት መጋበዝ መሆኑም ተገልጿል፡፡

 

ሁለት የአላባማ ካውንቲ ፍርድ ቤቶች ውሳኔውን ውድቅ በማድረግ ምንም አይነት የተመሳሳይ ጋብቻ የምስክር ወረቀት የማይሰጡ መሆናቸውን ገልጸው ከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ዳግም እንዲያጤነው ጠይቀዋል። ከዚህም በተጨማሪ የቴክሳስ ከፍተኛ አተርኒ ተመሳሳይ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን በግለሰብ ነጻነት ስም ሰዎች ሰብአዊ ክብራቸውን እንዲያዋርዱ መፍቀድ የለብንም የሚሉ አሜሪካውያን በየግዛቱ ተቃውሞ በማሰማት ላይ ናቸው። አንድ ታዋቂ የቤተክርስትያን ፓስተር በበኩላቸው በሚያገለግሉበት […]

32ኛው በሰሜን አሜሪካ በድምቀት እየተከበረ የሚገኘው የኢትዮጲያዊያን የሰፖርትና የባህል ፌስቲቫል ላይ ከተዘጋጁት ዝግጅቶች መሀከል በጉጉት የሚጠበቁት የሃሙስ እና የዓርብ የሙዚቃ ዝግጅቶች በወጣላቸው ፕሮግራም መሰረት እንደሚደረጉ ተረጋገጠ። ቴዲ አፍሮና ጎሳዬ ተስፋዬ ቪዛቸውን ለማግኘት የአሜሪካ ኤምባሲ የሲስተም መበላሸት ያዘገየው ቢሆንም አሁን ከደቂቃዎች በፊት ኤንባሲው ችግሩን እንዳስተካከለ የሚከተለውን መግለጫ አውጥቷል። U.S. Embassy Addis Ababa በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካን […]