የሐረር ሕዝብ ብሶቱ ቀጥሏል፡፡ አዲስ አበባ ያሉ ባለሥልጣናትም ዝምታቸው ቀጥሏል፡፡
በሃረር የህዝብ ብሶት ይገነፍላል የሚል ስጋት አይሏል::የሃረሪ ብሄራዊ ሊግ በዘር ማንዘር የተሳሰረ የሙስና ሰንሰለት ዘርግቷል::የምንሊክ ሳልሳዊ ዘገባ::

በሃረሪ ብሄራዊ ሊግ የሚመራው የሃእርሪ ህዝብ ክልላዊ መንግስት እያለ ራሱን የሚጠራው ወያኔ ሰራሹ የጎሳ ጁንታ በሃረር እና አከባቢው ህዝብ ላይ ከፍተኛ በደሎችን እየፈጸመ እንዲሁም ሃገርን እና ህዝብን እየዘረፈ በሙስና እና በመልካም አስተዳደር አጣብቂኝ ውስት ተዘፍቆ ህዝቡን እያስለቀሰ መሆኑን ከአከባቢው የሚደርሱ መረጃዎች ይጠቁማሉ::

በሐረር የሚገኙት የክልሉ ባለስልጣናት ዋና ግባቸው ስለልማትና ስለ መልካም አስተዳደር ሳይሆን ዘርፎ ስለመክበር እና በጫት ሱስ እግርን አጣጥፎ ከቤት ተጎልቶ መዋል ከሆነ አመታቶች ተቆጥረዋል፡፡ የክልሉ መንግስት መዋቅር በጎሳ የተቆጣጠረ በዘመድ አዝማድ፣ በዘር የተያያዘ በመሆኑ ማን ለማን ጥያቄውን አቤቱታውን እና ብሶቱን ማሰማት እንዳለበት አስቸጋሪ ሆንዋል፡፡ ከዚህ ቀደም አዛውንቶችን በመደብደብ ሰውን ከነህይወት በማቃጠል እና ፍርድ በማጓደል እንዲሁን ከባድ ወንጀሎችን በመስራት የተካነው የሃረሪ ብሄራዊ ሊግ እና አባሎቹ እንዲሁም የኦሕዴድ ተጠሪዎች ማሰር፤ ማባረር በፍርድ ቤት ማስወሰን፣ መቀማት፣ በልዩ ኃይል ማስደብደብ የመሳሰሉትን ድርጊታቸው የእለት እለት ተግባር ስለሆነ ሕዝቡ ለምዷቸዋል፡፡ በሃረር በጎሳ እና ካልተሳሰሩ የገንዘብ ሰንሰለት ካሌለ ባለሀብት የመሆን እድሉ የለም ፡፡ ማንኛውም ነገር የሃሰት እና የይስሙላ ነው፡፡ ለሐረሪ ብሔራዊ ሊግ ገንዘብ ካልከፈለ ባለሀብት መባል ዘበት ነው::

ክልሉ የህዝቡን ትርታ ለማዳመጥ በሚል ለይስሙላ በጠራው ስብሰባ ላይ የተለያዩ ድርጅቶችና የኅብረተሰብ ክፍሎች በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ተሰባስበው ውይይት በተደረገበት፣ የክልሉን ጉድፍ ያጋለጡና የተናገሩ ግለሰቦች በማግሥቱ የሥራ ዕገዳና ማስጠንቀቂያ እንዲደርሳቸው መደረጉ ነው፡፡ በውይይቱ ላይ የህዝብን ብሶት ያሰሙ የመብት ረገጣ ዛቻ እና ስድብ ደርሶባቸዋል እየደረሰባቸውም ነው::

ይህንን ዘገባ ያጠናከረው ምንሊክ ሳልሳዊ እንዳለው ከከተማው የተሰበሰቡ የህዝብ አስተያየቶች እንደሚጠቁሙት በሐረሪ የህግ ትርጉም በተግባር ሳይሆን በሃሰት-የህዝብ እድገት በጋራ ሳይሆን በወረቀት እና በጎሳ ነው፡፡ ከከፍተኛ የክልሉ አመራር ጀምሮ እስከቀበሌ ሹማምንት በውሸት የተሞሉ ናቸው::ዘረኝነትና የጎጥ መጠራራት ገንኖ፣ የጎሳ ፖለቲካ አክራሪነት ተስፋፍቶ፣ የሰው መብት እንደ ትቢያ በሚበተንበት ክልል፣ መልካም አስተዳደር አለ ተብሎ በፌዴራሉ ቱባ ባለስልጣናት መነገሩ የሚያስተዛዝብ ነው፡፡ ከማእከላዊ የመንግስት ቢሮዎች የሚመጡ የፌዴራሉ ባለስልጣናት የሚቀርብላቸውም ሆነ ይዘውት የሚሄዱት ሪፖት እጅግ አስደንጋጭ መሆኑ እየታወቀ የፌዴራል ባለስልታናት ዝምታ የፖለቲካ ስልጣን ማስጠበቂያ አስመስሎታል:: ህዝብን የሚያዳምጥ አስተዳደር ያጣው የሃረር ነዋሪ ቁጣው ገንፍሎ አደባባይ ሊወጣ ይችላል የሚል ስጋቱ አይሏል::የምንሊክ ሳልሳዊ ዘገባ::

በኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን የድህረምረቃ ተማሪዎች የኢትዮጵያን የፕሬስ ሁኔታ በልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስት ውስጥ የሚኖረውን ሚና በተመለከተ የአንድ ቀን የውይይት መድረክ አዘጋጅተው ነበር።

መድረኩ ዘግየት ብሎ ቢጀመርም የተጠናቀቀውን ግን ከምሽቱ አንድ ሰዓት አካባቢ ነው። የውይይቱ ሙቀትና ግለት በፈጠረው ስሜት የሻይና ቡና እረፍትን ያስፈለገው አልነበረም። በውይይቱ ላይ በርካታ ርዕዮተ ዓለማዊ መፋጨቶችና ጉንተላዎች የታዩበት ነው። ውይይቱ በዋናነት ኢህአዴግ እመራበታለሁ በሚለው “ልማታዊ ዴሞክራሲ” አስተሳሰብ ውስጥ የፕሬሱ ሚና ምን እንደሆነ ለማየት ቢፈለግም፤ ውይይቱ ግን ኢህአዴግና አንድነት ፓርቲ የሚሟገቱበት እንዲሁም ዶ/ር ዳኛቸውና አሰፋና የመንግስት ኮሙኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በኀሳብ የተጎሻሸሙበት፣ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው የፓርቲያቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ የሞከሩበት፤ አቦይ ስብሃትና አቶ ዛዲግ አብርሃ በበኩላቸው የኢህአዴግን ጥቅም ላለማስነካት የተፋለሙበት፤ ሁሉም ተፃራሪ ኃይሎች በአንድ ቦታ ተገኝተው የሃሳብ ፍልሚያ ያደረጉበት መድረክ ነበር ለማለት ይቻላል። ውይይቱ የተቃራኒ አስተሳሰብ ባላቸው ወገኖች የሚደረግ ቢሆንም፤ ዶ/ር ዘነበ በየነ መድረኩን ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መርተውታል።

በውይይት መድረኩ የተገኙ፣ ጥናት ያቀረቡ ወገኖች የአሰላለፍ መስመራቸው ከወደ ገዢው ፓርቲ የሚያደሉ ቢመስሉም፤ ከተሳታፊዎች ተነስተው የነበሩ ኀሳቦችም ሚዛናቸው ከፍተኛ ስለነበር ውይይቱ ውጥረት ይታይበት ነበር። በመጠኑም ቢሆን የምርጫ 97 የምርጫ ክርክር የሚያስታውስ ይመስል ነበር። በምርጫ 97 ወቅት የኢህአዴግ ተከራካሪዎች በኀሳብ እጥረት ቢበለጡም በእሁድ ዕለቱ ውይይት ላይ ግን ለኢትዮጵያ የሚበጀው መንግስታዊ ስርዓት “ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ” ነው ሲሉ ተሟግተዋል። በአንፃሩ “ልማታዊ ብሎ ዴሞክራሲ” የለም በሚል ከፍተኛ የሆነ የኀሳብ ትንቅንቅ የታየበት ነበር።
የዕለቱ ዋነኛው መከራከሪያ በልማታዊ ዴሞክራሲ ስርዓት ውስጥ የሚዲያው ሚና ምን መሆን እንዳለበትና በዚሁ ርዕሰ ጉዳይ እንዲያተኩር ቢፈለግም ፖለቲካዊ ክርክሩ የጎላበት ነበር።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ቤት ኃላፊ ዶ/ር አብዲሳ ዘርአይ ለመወያያ ባቀረቡት ጽሁፍ ላይ የልማታዊ መንግስት አስተሳሰብ ከሩቅ ምስራቅ ሀገራት ማለትም ከደቡብ ኮሪያ፣ ከታይዋንና ከጃፓን የሚቀዳ አስተሳሰብ መሆኑን በመጠቆም የአስተሳሰቡን ተግዳሮቶች ወገናዊ ባልሆነ (Neutral) መንገድ አቅርበውታል። “የልማታዊና ዴሞክራሲያዊ” የሚለውንም የኢህአዴግ መስመር ብዥታ ያለበት አካሄድ መሆኑንም በስሱ ገልፀውታል። ከሁሉም በላይ ልማታዊም ተባለ ዴሞክራሲያዊ ቢያንስ ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጋራ ሊያግባባ የሚችል፣ ሀገራዊ መግባባት (National Consensus) አስፈላጊነትን ደጋግመው ገልፀዋል። ዶ/ር አብዲሳ ከፖለቲካ ጋር በተያያዘ ከ400 በላይ ሰዎች ታስረዋል በሚባልበት ሀገር ይሄንን ገዢ ሀሳብ ወገናዊ ባልሆነ መንገድ ማንፀባረቃቸው በተወያዮች ዘንድ በበጎ እንዲታይላቸው አድርጓል። ይሁን እንጂ ዶ/ር አብዲሳ ለብሔራዊ መግባባት “የታሰሩ ይፈቱ፣ በውጪ የተሰደዱም ይመለሱ፣ መንግስትና ተቃዋሚዎች ያለቅድመ ሁኔታ ይደራደሩ” በሚል መጠን (Tone) ቢናገሩት የተሻለ እንደነበረም መገመት ይቻላል። ለዚህም ይመስላል የዶ/ር አብዲሳን የመወያያ ጽሁፍ አፍቃሬ የገዢው ፓርቲ ተወያዮችንና ተቀዋሚዎችን ያላጠገበው።

የፋና ብሮድካሰት ኮርፖሬት አክሲዮን ማኅበር ሥራአስኪያጅ በዕለቱ የመወያያ ጽሁፍ ካቀረቡ አንዱ ነበሩ። ስራ አስኪያጁ አቶ ወልዱ ይምሰል ሚዲያው በልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ውስጥ በሚፈጠረው ፖለቲካል ኢኮኖሚ ውስጥ ወሳኝ ተሳትፎ ከሌለው በቀር ሚናውን መወጣት እንደማይችል በመግለፅ አሁን ያለውን ሚዲያ ተችተዋል። በተለይ የግል ሚዲያውን አነሳስና አመጣጥ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ ገልፀውታል። አቶ ወልዱ ሚዲያው በዴቨሎፕመንታል ዴሞክራሲ ውስጥ ንቁ ተሳታፊ ለመሆን የፋና ብሮድካስትን ሞዴል የሚመስል ነገር ተናግረዋል። በዕለቱ በስብሰባው ላይ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ወክለው የተገኙት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ በአሁኑ ወቅት ያለው የፖለቲካ ኢኮኖሚ ሳይሆን የፖለቲካ ስልጣን ወይም ኃይል (Political Power) ነው በማለት የአቶ ወልዱን ጥናት በአጭር ቃል መትተውታል።

ዶ/ሩ በዕለቱ እንደተናገሩት ዩኒቨርሲቲው ከመሰረቱ (Public) የሕዝብ ቢሆንም የግል (Private) ሆኖ ከመቆየት መጥቶ አሁን ሕዝባዊ የበላይነት ይዞ በመጣበት ጊዜ ውይይቱ መካሄዱን አወድሰዋል። ነገር ግን በውይይቱ ላይ ሁሉም አካላት አለመጋበዛቸው ወይም ግብዣው ያላረካቸው መሆኑን ሳይናገሩ አላለፉም። በውይይቱ የተሳተፉ አካላት ሚዛናዊ አለመሆኑንም ለመጥቀስ የገብረክርስቶስ አባትን ተረት የአለቃ ደስታ ነገዎ የመጀመሪያው የአፄ ኃይለስላሴ ፓርላማ ሲቋቋም አፄ ኃይለስላሴ የፓርላማው ተሰብሳቢዎችን ከአንድ ወገን መሆናቸውን በማየት (እነዚህ ሰዎች የሚመክሩ ወይስ የሚመከርባቸው) በማለት የውይይቱ ተሳታፊዎች ሚዛናዊ አለመሆን ጠቅሰዋል። ከዚሁ የተሳታፊዎችና አቅራቢዎች ሚዛናዊ አለመሆን ጋር በተያያዘም “አንዳንድ ሚኒስትር ዲኤታዎችን በማይበት ጊዜ” በማለት የአቶ ሽመልስ ከማልን በውይይቱ ላይ መገኘት ጥያቄ እንዳጫረባቸው ጠቅሰዋል።
የዶ/ር አብዲሳን የማወያያ ጽሁፍን ዶ/ር ዳኛቸው ሲያሄሱም በልማታዊ መንግስትነትና በዴሞክራሲያዊ መንግስት መካከል ውጥረት (Tension) አለ ማለታቸውን እንደሚስማሙበት ገልፀዋል። በደርግ ጊዜም እኩልነት ከነፃነት (Equality Vs Liberty) የተፋጠጡበት በመሆኑ ደርግ የዜጎችን ነፃነት ጨፍልቆ እኩልነት ሊያመጣ ፈለገ ብለዋል። በእሳቸው አገላለፅ “አሁን የመጣብን ጉድ” ያሉት ልማትን በበላይነት ይወስድና ነፃነትን (Liberty) ይጨፈልቃል። ኢህአዴግ አሁን የሚመራበት “ልማታዊና ዴሞክራሲ የፈለጋችሁትን ያህል ብትባባሉት አይታረቅም ብለዋል።

በመቀጠል የተናገሩት አቦይ ስብሃት ነበሩ። የአቦይ ስብሃት ምላሽ ለዶ/ር ዳኛቸው መልስ የሚመስል ነበር። በአቦይ ስብሃት እምነት ልማት እንደ አይዲዎሎጂ የሞት ሽረት ጉዳይ ነው። የመኖር ወይም ያለመኖር ነው። በአቦይ እምነት ልማት የዴሞክራሲ መሰረት ነው። የዴሞክራሲ ኃይሎች የሚባሉ ባለሃብቱና ላብ አደሩ ናቸው። ሌሎቹ የደጋፊነት ሚና ሊኖራቸው ይችላል። ልማት የእንጀራና የቤት ጉዳይ ሳይሆን የፀጥታ ጉዳይ ነው። ልማት ያለ ዴሞክራሲ አይሄድም። ቢያንስ ባለው ሁኔታ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መፈቀድ ስላለባቸው። ኢህአዴግ በሕገመንግስቱ እነዚህን መብቶች አስቀምጧል። እነዚህም የመነጋገር የመፃፍና የብሔር እኩልነት ናቸው ብለዋል።

“ልማትና ዴሞክራሲ አይነጣጠሉም” የሚለውን ደግሞ አቶ ስብሃት ሲያስረዱ “አንዱ ያለ ሌላው ሊኖር አይችልም” ብለዋል። በኢትዮጵያ ልማት ከሌለ ዴሞክራሲ የለም። ሁለቱም ተባብረው መሄድ አለባቸው ብለዋል። እንደ አቦይ ሰብሃት ገለፃ በሀገሪቱ የዴሞክራሲ መገለጫዎች አንዱ የነፃ ገበያ ስርዓት ነው። ነገር ግን የነፃ ገበያ አስተሳሰብና ኢህአዴግ የተዋወቁት በድንገት ነው። አቦይ ስብሃት የተገናኙበትንም አጋጣሚ ሲገልፁ፤ “መጀመሪያ የነበርነው ሶሻሊዝም ነበር። ነገር ግን ወደ ካፒታሊዝም እንዙር ተብሎ ነገሩ ሲጠና ሰዎች ወደ ውጪ ልከን፣ መፃህፍት ከውጪ አምጥተን ነበር። ይሄ ካፒታሊዝም የሚባል ነገር ምን እንደሆነ በሀገሪቱም ሆነ እኛም እንደ ድርጅት አናውቀውም። ነፃ የኢኮኖሚ ባዕዳዊ እንሰሳ በመሆኑ ይሄንን ባዕድ እንሰሳ ለማጥናት ብዙ ጊዜ ወስዶብናል። በደርግም ቢሆን የነፃ ገበያ አስተሳሰብ ብዙ ሰው አስገድሏል። ኢህአዴግም ነፃ ገበያን ለማጥናት በአራቱም አቅጣጫ ሰው ልኮ በታላቅ እሩጫ አስጠንቷል” ብለዋል። ከዚያም ወደ ዴቨሎፕመንታል መንግስት ማምራቱንና በእሳቸው ቃል በቃል አገላለፅ “የመንግስት እጅ ያለበት ነፃ የኢኮኖሚ ስርዓት” መመስረቱን አስረድተዋል። ስለሆነም መንግስት በጥንቃቄ በተመረጡ ጉዳዮች ገበያው ሊፈፅማቸው በማይችል መስኮች እጁን ያስገባል። ልማታዊ ዴሞክራሲ መንግስት ማለት ይሄው ነው ብለዋል። መንግስት እጁን ያላስገባበት ካፒታሊዝም እንደሌለ በመናገር የእንግሊዝም ሆነ የአሜሪካ መንግስታት ልማታዊ መንግስታት እንደነበሩም ተናግረዋል።
በመቀጠል መነጋገሪያው ወደ አንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወጣቱ ፖለቲከኛ ሀብታሙ አያሌው ነበር። አቶ ሃብታሙ አገዛዙ በልማታዊ መንግስት ባህሪይ ስም እንቅፋት ናቸው ያላቸውን በማጥፋት የተመሠረተ በመሆኑ ለዴሞክራሲያዊ ሂደት መፈናፈኛ የማይሰጥ ስርዓት ነው ብሎታል። እስካሁንም ድረስ አንዱን ከአንዱ ከማምታታት ባለፈ ኢህአዴግ ስለልማታዊ መንግስት ግልፅ አለመሆኑን ጠቅሷል። በተለይ ከ1993 ዓ.ም “ተሃድሶ” በኋላ የመጣው የኢህአዴግ ባህሪ ልማታዊ አስተሳሰብን እያቀነቀኑ በስልጣን ላይ በመቆየት ገዢ የመሆን ፍላጎት መኖሩን፣ ልማት የሕዝቡና የሀገር ሳይሆን የገዢው ፓርቲ ህልውና ተደርጎ መታየቱን ከግምት የሚያስገባ እንደሆነና በዙሪያው ደግሞ እንቅፋት ይሆናሉ ብሎ የሚያስባቸውን ገለል በማድረግ፣ አስቀድሞ ይዞት በመጣው የፖለቲካ ባህሪው የሚነሳውን ማንነቱን በጉልበት እያሰፈነ የሚሄድ ስርዓት ነው ብሎታል።

ይሄ ስርዓት ደግሞ የቱንም ያህል ተሻግሮ ተሻሽሎ ቢመጣ ልማታዊ ባህሪውን ይዞ ለስልጣኑ እንቅፋት የሚሆኑትን በጠላትነት ፈርጆ መንቀሳቀሱን የጠቀሰው አቶ ሀብታሙ በዚህ ረገድ የግል ሴክተሩን ከማቀጨጭ ባለፈ ምሁራንን በጥርጣሬ እንደሚያይና የግል ሴክተሩን በፖለቲካ ካድሬ ከመምራት ባለፈ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ወደ ዳር ማግለሉን ጠቅሷል። ኢህአዴግ ሁሉንም አገልግሎ እያለ የተለየ ኀሳብ መስተናገድ ባልቻለበት ሁኔታ ዴሞክራሲ እንዴት ሊኖር ይችላል ሲልም ጠይቋል።

“ኢህአዴግ ከእኔ የተለየ አስተሳሰብ የያዘ በሙሉ መጥፋት አለበት ብሎ የሚያምን ስርዓት እንዴት አድርጎ ዴሞክራሲያዊ ግን ደግሞ ልማታዊ የሚሆነው” የሚለው አቶ ሀብታሙ አሁንም በልማትም ሆነ በወሳኝ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ያስፈልጋል ብሏል።
የግል ሚዲያውን በተመለከተ የሬዲዮ ፋና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ወልዱ እና አቦይ ስብሃት የሰጡትን አሉታዊ አስተያየት በተመለከተም አቶ ሃብታሙ ምላሽ ሲሰጥ የሚሚ ስብሃቱን ሬዲዮ ጨምሮ በመንግስት ቁጥጥር ስር ያሉ የሕዝብ የመገናኛ ብዙሃን ፍርድ ቤት ባልወሰነበት ሁኔታ በሕግ ተመዝግበው የሚንቀሳቀሱትን ተቃዋሚ ፓርቲዎች “አሸባሪ ናቸው” እንደሚሉ በመግለፅ ከግሉ ሚዲያ በላይ መወቀስ ያለባቸው መሆኑን ጠቅሷል። በጥቅሉ በሂደት ይመጣል የተባለው ዴሞክራሲ ሂደቱ እየተደናቀፈ በሂደት ይመጣል ማለት ዘበት ነው። በርካታ ጋዜጠኞችንና ፖለቲከኞችን እስር ቤት ወርውሮ ለብቻው እየፈረጠመ ያለ መንግስት ልማታዊ ባህሪ የለውም፣ የግሉ ሴክተር ከጠቅላላው የሀገሪቱ ሀብት ጂ.ዲ.ፒ 5.6 በመቶ በያዘበት አሳፋሪ ሁኔታ ፈጣን ልማት ሊረጋገጥ አይችልም። በኢትዮጵያ የግል ዘርፍ እድገት የልማት ብቻ ሳይሆን የዴሞክራሲ ጉዳይ ነው። የግል ዘርፉ በቀጨጨበትም ልማት አይመጣም። የግል ዘርፉን የሚያቀጭጭ፣ ምሁሩን የሚጠራጠርና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን “አሸባሪ” የሚል ስርዓት ልማታዊ ሊሆን አይችልም ብሏል። የፖለቲካ አለመረጋጋት ከመፈጠሩም በፊት ኢህአዴግ ከዚህ ባህሪው መውጣት እንዳለበትም ገልጿል። ለዴሞክራሲ ማበብ ወሳኝ የሆኑ ተቋማት ነፃነታቸው ማረጋገጥና ሚዲያውም መሀል ላይ ቆሞ ኅብረተሰብ የሚያገለግል መሆን አለበትም ሲል አስረድቷል።

አቶ ዛዲግ አብርሃ በዚሁ ጉዳይ ላይ ለውይይት የሚሆን ጽሁፍ ከማቅረባቸው ባሻገር ልማታዊነትና ዴሞክራሲያዊነት የማይነጣጠሉ መሆናቸውን ለማስረዳት ብዙ ብለዋል። አቶ ዛዲግ እምብዛም በሕዝብ የማይታወቁ (public personality) ባይኖራቸው በየጥናታዊ መድረኩ የኢህአዴግን አቋም ከሌሎች በተሻለ የሚያቀርቡ ወጣት ፖለቲከኛ ናቸው። በአሁኑ ወቅት የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ምክር ቤት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ የሚለውን የገዢው ፓርቲ አስተሳሰብ ለማስረዳት “የማይታረቅ ነው” የሚለውን የዶ/ር ዳኛቸውን፣ የዶ/ር ነጋሶን፣ የዶ/ር ያዕቆብን የአቶ ሀብታሙንና እንዲሁም የዶ/ር አብዲሳን የጥርጣሬ አቋም “የሚታረቅ ነው” በሚል የኮሪያና የታይዋንን ልምድ በማንሳት ለማስረዳት ጥረት አድርገዋል። ኮሪያና ታይዋን ልማታዊ መንግስታት ቢሆኑም ዴሞክራሲያዊ አለመሆናቸውን፣ ለዚህም ምክንያቱ የመጀመሪያው ደሞክራሲያዊ ላለመሆን ማስቻያ ምክንያት (enabling environment) መኖሩ ነው። ይኸውም በደቡብ ኮሪያም ሆነ በታይዋን ብዝሃነት አለመኖሩ፣ ሁለተኛው አርሦ አደሩ እርስ በርስም ሆነ ከገበያ ጋር የተገናኘ commercialized ስላልነበር መንግስትን የመቃወም ችሎታ አልነበረውም። እንዲሁም በወቅቱ ያሉት የደቡብ ኮሪያና የታይዋን መንግስታት ዴሞክራሲያዊ ያለ መሆን ፍላጎት (will) ነበረባቸው። ዴሞክራሲያዊ ያለመሆን ፍላጎታቸው የመጣው ደግሞ አክራሪ የቀኝ ኃይል (far right movement) በመሆናቸው፣ ሕዝባቸውን የሚጠራጠሩ መንግስታት ስለነበሩና ለአርሶ አደሩ መሬት አከፋፍለውትም ቢሆን አያምኑትም። እንዲሁም የሚፈሩት ሌላ ውጫዊ ጠላት የቻይና እና የሰሜን ኮርያ መንግስት ነበር። በእነዚህ ምክንያቶች ልማታዊ ቢሆኑም ዴሞክራሲያዊ አልነበሩም። ነገር ግን በሂደት ወደ ዴሞክሪሲ የተቀየሩት ተበትኖ የነበረው አርሶ አደር ምርት እየጨመረ ሲሄድ Commercialized ሲሆን፤ እርስ በርሱ በመገናኘቱ ለጭቆና የማያመች መሆኑ፤ በሌላ በኩል የመንግስታቱ ዴሞክራሲያዊ ያለመሆን ባህሪ የሶቪየት ኅብረት መፍረሱን ተከትሎ የሚፈሩት ጠላት ስላልነበረና የfar right movement ወደ መሀል መምጣቱን ተከትሎ ወደ ሶሻል ዴሞክራሲ መምጣት በመጀመራቸው ነው ይላሉ።

አቶ ዛዲግ ወደ ኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ሲመጡ በመጀመሪያ ፖለቲካ ኢኮኖሚው በገበያ ያልተሳሰረ አርሦ አደር በመኖሩ ዴሞክራሲያዊ ላልሆነ አስተዳደር ሊመች ቢችልም በሀገሪቱ ከፍተኛ ብዝሐነት አለ ብለዋል። በሀገሪቱ የብሔር የሃይማኖተና የጾታም ብዝሃነት በመኖሩ። ይሄንን አቻችሎ ለመምራት ዴሞክራሲያዊ መሆን አስፈላጊ ነው ብለዋል። በእሳቸው አባባለ ብዝሀነትን ማስተናገድ ባለመቻላችን ከመፍረስ ጫፍ ደርሰን ተመልሰናል ብለዋል። ከዚህ አንፃር አሁን ያለው ስርዓት Undemocratic አይደለም ብለዋል።

በሌላ በኩል አሁን ያለው መንግስት ፀረ-ዴሞክራሲ የመሆን ፍላጎት (will) የለውም ብለዋል። ለዚህ ኀሳባቸው ደግሞ እንደ መከራከሪያ ያቀረቡት ታጋዮች ለልማት፣ ለመልካም አስተዳደርና ለዴሞክራሲ ስርዓት ትምርታቸውን አቋርጠው በሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ለሞት ገብረው ያመጡት ስርዓት ነው ብለዋል። “ኢህአዴግ አክራሪ የቀኝ ኃይል አይደለም። ኢህአዴግ ሕዝቡን የሚጠራጠርና አርሶ አደሩን የሚፈራ አይደለም። የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትራችን እንዳሉት አርሶ አደሩ በሸካራ እጁ እቅፍ ድገፎ ያደርሰው አርሶ አደሩ ነው። እና ኢህአዴግ በአርሶ አደሩ ተፈጥሮ በአርሶ አደሩ እዚህ የደረሰ ሰርዓት ነው” ብለዋል። እንደታይዋንና ኮርያም የሚፈራው ሊውጠው የተዘጋጀ የጎረቤት መንግስት የጦርነት ስጋት ስለሌለበት በማንኛውም መመዘኛ ኢህአዴግ ፀረ-ዴሞክራሲያዊ የሚሆንበት ዕድል የለውም።
በርዕሰ ጉዳዩ ላይ ከላይ የተጠቀሱት ተናጋሪዎች ኀሳብ ተጨምቆ ሲታይ ሁለቱ አስተሳሰቦች የሚታረቁበት መስመር ቁልጭ ብሎ የወጣ አይመስልም። ኢህአዴግ ልማት ቢልም እየተካሄደ ያለው ልማት በዋናነት በቻይና መንግስት ብድርና እርዳታ የሚካሄድ መሆኑና ከኅብረተሰቡ የልማት ጥያቄ አንፃር አርኪም በቂም አለመሆኑ በሌላ ወገን ደግሞ ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በተመለከተ በሕዝቡም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሀገሪቱ ያለችበት ተጨባጭ ሁኔታ አስጊ መሆኑ የኢሕአዴግን “ልማታዊ ዴሞክራሲ” ብዥታዊነት ይበልጥ ያንፀባረቀ የሚመስል ነው። ኢህአዴግ በንድፈ ኀሳብ የደቦና የመብትን ጥያቄ ሳይነጣጠሉ አስኬዳለሁ ሲል ተቃዋሚዎቹ ደግሞ መብት ይረጋገጥና ከዛ ደቦው (ልማቱ) ይከተላል የሚል ኀሳብ እያንፀባረቁ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል። በዚያኑ ዕለት አንድ ወጣት የዩኒቨርስቲ ተማሪ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር “የኢትዮጵያ ሕዝብ ዳቦ ወይስ ነፃነት ቢሉት ነፃነትን ይመርጣል” ማለታቸውን በማስታወስ ግራ መጋባቱንም ገልጿል።

በዕለቱ ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር ተቀራራቢነት ያለው የውይይት ኀሳብ ያቀረቡት አቶ ሞሼ ሰሙና የፎርቹን ጋዜጣ ማኔጂንግ ኤዲተር ታምራት ገ/ጊዮርጊስ ነበሩ። ሁለቱንም አቅራቢዎች በልማታዊ ደሞክራሲያዊ ስርዓት ውስጥ የፕሬሱን ፈተና ዘርዝረዋል። በተለይ የአቶ ሞሼ ሰሙ ኀሳብ የፕሬሱ የአነሳስ ችግርና የመንግስትን ጫና በማያወላዳ ሁኔታ ጠቅሰውታል። ብዙዎቹ ተሳታፊዎች የአቶ ሙሼን ኀሳብ ዓይንን በማይስብ ማሸጊያ እንደታሸገ ግን ደግሞ ይዘቱ እንደሚጥም ብስኩት የመሰሉትም ነበሩ። የአቶ ሞሼን የጥናት ሃሳብ በሌላ ጊዜ የምንጠቃቅሰው ይሆናል።

ጋዜጠኛ ታምራትም ለጋዜጠኝነት ሙያ ሉአላዊነት ተሟግቷል። ሙያውን ፖለቲከኞች በራሳቸው አሰላለፍ ለማካተት የሚሄዱበተን ጥረት ትክክል እንዳልሆነ ገልጿል። የጥናት ኀሳቡ ከሕገ-መንግስቱ አንፃር በመሆኑ ሕገ-መንግስቱ የነፃነት ሰነድ (Liberal Document) እንደሆነ አስገንዝቧል። ምንም እንኳ በሕገ-መንግስቱ የመልማት መብትንና የብሔር ብሔረሰብ የቡድን መብትን በመጥቀስ ወደ ልማታዊ ሕገ-መንግስት የሳቡት ቢኖሩም ታምራት ግን ሕገ-መንግስቱ መሠረታዊ የመናገር፣ የመፃፍና ሌሎች የግለሰብ መብቶችን በበቂ ሁኔታ ያካተተ በመሆኑ የነፃነት ሰነድ በማለት ኢህአዴግና ደጋፊዎቹ ከልብ ወደማይወዱት ሊብራሊዝም ስቧቸዋል።

ጋዜጠኛ ታምራት በስራ ላይ ያለውን ሕገ-መንግሰት በውስጡ የተካተቱትን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በማስላት፣ የመገንጠልና የቡድን መብት ጥያቄዎችን እንደሌሉ በመቁጠር `Liberal Document` ነው በማለቱ ተቃውሞ የቀረበበት ከኢህአዴግ ወገን ብቻም አልነበረም። ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ “አንተ ለሀብታም ስለምትፅፍ ነው” በሚል ኃይለቃል ፖለቲካ ቢፅፍ ኖሮ የችግሩን ገፈት ይቀምስ እንደነበር በገደምዳሜም ቢሆን አስተያየት ሰጥተውታል። ዶ/ር ዳኛቸው ታምራት ሕገ-መንግስቱ “የነፃነት ሰነድ ነው” ያለበት አገላለፅ የፖለቲካ ጉዳዮችን ፅፎ ቢሆን ኖሮ ይሄንን ቃል በሙሉ ልብ አይጠቀምም ከሚል መነሻ ሊሆን ይችላል። ያም ሆኖ በጋዜጠኛ ታምራት እምነት ሕገ-መንግስቱ የነፃነት ሰነድ ቢሆንም በአስፈፃሚው የሚወጡ ሕጎች ግን ሕገ-መንግስቱን የዘነጉ መሆኑንም ሳይጠቅስ አላለፈም።

በመጨረሻ የተናገሩት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ ለዶ/ር ዳኛቸው መልስ የሰጡበት ነበር። አቶ ሽመልስ ዶ/ር ዳኛቸው ነፃ ፕሬስ የለም ማለታቸውን “ደፋር” በሚል አገላለፅ ከመቱት በኋላ “ኀሳባችንን የምንገልፅበት መድረክ አጣን” የሚለውን የዶ/ሩን ቅሬታ ከእኛ በላይ የመጽሔትና የጋዜጣ ፊት በየዕለቱ እየወጡ እንደልባቸው የሚያጨናንቁ ሰዎች ኀሳባችንን መግለፅ አልቻልንም ማለታቸው ቅጥፈት መሆኑን በመግለፅ ሚኒስትር ዴኤታው በሀገሪቱ ነፃ ፕሬስና ኀሳበን የመግለጫ መሳሪያ ችግር እንደሌለ ተናግረዋል።

በአጠቃላይ የውይይት መድረኩ የተሟሟቀ ነበር ማለት ይቻላል። በርካታ ሃሳቦችም ተፋጭተዋል። በጥቅሉ ፕሮፌሰር አብይፎርድ በመጨረሻ እንዳሉት የዴሞክራሲ ተራራ እየወጣን ነው ብለዋል። ተራራው ትክክል መሆኑን ማመን አለብን። አልፎ አልፎ ግን በውይይት ወቅት ሻካራ ስሜት ሊፈጠር፣ ሊኮሰኩስም ይችላል። ስለዚህ ዴሞክራሲያዊም ሆነ ልማታዊ ስንል ብዙ ጣጣ አለው። እነዚህን ችግሮች ክፍት በሆነ ውይይት ማስኬድ ነው። በመጨረሻም ዴሞክራሲያዊ በሆነ መርህ የሚደረግ ውይይት በፈላጭ ቆራጭ ቋንቋ መሆን የለበትም ብለዋል
በዘሪሁን ሙሉጌታ

አራተኛው ሰው ጉድ አፈሉ!(ጋዜጠኛ መስፍን ኣብርሃ – ጀርመን)goolgule

Image

ኢትዮጵያና አሜሪካ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ከጀመሩ ዘንድሮ 111ኛ ዓመታቸውን ይዘዋል። በቀድሞው የኢትዮጵያ ንጉስ አፄ ምንሊክና በአሜሪካው አቻቸው ፕሬዚዳንት ቴዎዶር ሩዝቬልት ልዑካን መካከል ለዘጠኝ ቀናት ድርድር ከተካሄደ በሁዋላ ነበር ግንኙነቱ በይፋ የተጀመረው። ከአንድ ክፍለ-ዘመን በላይ ያስቆጠረው የአገራቱን ግንኙነት በመጠቀም ኢትዮጵያ ጠቀም ያለ እርዳታዎችን ተቀብላለች።በአሁኑ ወቅትም በየዓመቱ ከ500 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ የልማትና የወታደራዊ እርዳታ ተጠቃሚ ናት። አሜሪካም ብትሆን ፖለቲካዊ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ከአገራችን ታገኛለች።ሆኖም ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ አሜሪካ በኢትዮጵያ ባሉ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር ዙሪያ ቅር መሰኘቷን ደጋግማ ስትገልፅ ቆይታለች። በየዓመቱ በአሜሪካ መንግስት ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሚወጣው የአገራት የሰብዓዊ መብት ሪፖርትም ኢትዮጵያ ባላት ሪከርድ በአሜሪካ ክፉኛ ስትተች ነበር።

ይህን ተከትሎም ይመስላል የአሜሪካ ህግ አውጪ ምክር ቤት/ኮንግረንስ ጥር 7/2006 ዓ.ም ባወጣው ዓመታዊ የበጀት ድልድል ቀመር ለኢትዮጵያ በሚሰጠው የልማትና ወታደራዊ ድጋፍ ላይ ቅድመ ሁኔታዎችን ያዘለ አንቀጽ ያካተተ ሕግ አፅድቋል።

ሕጉ የአገሪቱን ዓመታዊ የ2014 በጀት አሜሪካ እርዳታ የምትሰጣቸውን አገሮች እርዳታ ሰጪ ድርጅቶች የገንዘብ ተቋማት የሰብዓዊ መብት ተቋማትና የመሳሰሉትን በጀት ያካተተ ነው። በዚህ ዳጎስ ያለ ሕግ ላይ በአንቀጽ 70ሺ42 ገፅ 1ሺ294 ላይ የአሜሪካ መንግስት ለኢትዮጵያ የሚሰጠውን ወታደራዊና የልማት እርዳታዎች የሚመለከት ሆኖ እናገኘዋለን።

ከፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከምክትሉ ጆ ባይደን ከአሜሪካ የህግ አውጪ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ጆን ቤይነር ቀጥሎ የሴኔቱ ፕሬዚዳንት በስልጣን ተዋረዳቸው ደግሞ አራተኛው ሰው በመባል የሚታወቁት ከፍተኛ ሴናተርና ዴሞክራቱ ፓትሪክ ሌሂ አማካኝነት አንቀፁ እንዲካተት መደረጉ የሚገለፀው ይኸው ህግ እንደ ኦክላንድ ኢንስቲትዩት የማህበረሰብ ተቋም የፖሊሲ ዳይሬክተር ፍሬድሪክ ሙሶ ታሪካዊ ህግ ተብሎ እየተወደሰ ይገኛል።

ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ መንግስትን አስተዳደር የሚቃወሙትና ኤችአር 2003 በመባል የሚታወቀውን ህግ ያረቀቁት እንደራሴዎች ዶናልድ ፔይንና ክሪስ ስሚዝ በጉዳዩ ላይ ምንም አይነት እውቀት ሳይኖራቸው በአሜሪካ የሚገኙ የኢትዮጵያ መንግስት አግባቢዎች/ሎቢስት እንዲሁም በአምባሳደር ግርማ ብሩ የሚመራው በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ህግ አነፍናፊ አታሼዎች እውቅና በላይ ሳይታሰብ በድንገት ህግ ሆኖ የወጣው ይኸው አንቀጽ የሁለቱን አገራት መንግስታት ግንኙነት ሊፈታተነው እንደሚችልም ከወዲሁ ተገምቷል።

የህጉ አንቀጽ እንደሚያስገድደው የአሜሪካ መንግስት ለኢትዮጵያ የሚሰጠው እርዳታ በትክክል ለታለመለት ዓላማ መዋሉን የአሜሪካ ውጭ ጉዳይና የገንዘብ ሚኒስትሮቹ ማረጋገጥ አለባቸው። በጀቱ በስራ ላይ ከመዋሉም በተጨማሪ በጀቱን በቀጣይ ለመልቀቅ፤

ገለልተኛ ዳኝነት መኖሩን ማረጋገጥ ወይም ወደ ገለልተኛ ዳኝነት ለማምራት ጥረት እንደሚደረግ ውጤታማ እቅዶች በስራ ላይ መዋላቸውን ማረጋገጥ
የኢትዮጵያ መንግስት የመናገር ራስን የመግለፅ መብት መጠበቁን ሰላማዊ ስብሰባዎች ማካሄድን በእምነት ተቋማት ላይ ተፅዕኖ ያለማ ድረግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በነፃነት እንዲሰሩ ዜጎች ከህግ ውጭ የማይታሰሩና ማዋከብ የሌለ መሆኑን ማረጋገጥ
የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የመጎብኘት ዕድል እንዳይነፈጉ፤ በክልሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በፈፀሙ የፖሊስና የመከላከያ ሃይሎች ላይ ክስ እንዲመሰረት
በኦሞ ሸለቆና በጋምቤላ ክልል አካባቢዎች በሰፈራ ስም ዜጎች ከመሬታቸው እንዳይፈናቀሉና እንዳይሰደዱ ማረጋገጥ
ከአሜሪካ ህዝብ ቀረጥ ከፋዮች ተሰብስቦ ለኢትዮጵያ እርዳታ የሚውለው ገንዘብ የዜጎቹን ህይወት የሚያሻሽል እንጂ ድህነቱን የሚያባብስ እንዳይሆን ሁለቱም ሚኒስትሮች አረጋግጠው ለበጀት ኮሚቴው ሪፖርት ማድረግ እንዳለባቸው የህጉ አንቀጽ ያስገድዳል።

በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ስርዓቱ መሻሻልና የመልካም አስተዳደር መስፈንን በቅድመ ሁኔታነት የሚያስቀምጥ ህግ ነው ማለት ይቻላል።

ከዚህ ቀደም በሚሰጡ እርዳታዎች ላይ እርዳታውን ከመስጠት የዘለለ የቁጥጥር ነገር ስለማይደረግ ከፍተኛ ንብረትና ሃብት ተመዝብሯል የሚል ክስ የሚደመጥበት የኢትዮጵያ መንግስት ከአሁን በሁዋላ እያንዳንዷ ዶላር የት እንደዋለች የማሳመን ሃላፊነት ተጥሎበታል።

ሴናተር ሌሂ በተደጋጋሚ ጊዚያት በኢትዮጵያ ያለውን የሰብዓዊና የዴሞክራሲ መብቶች አያያዝ ላይ የተለያዩ ሪፖርቶችን አቅርበዋል። በተለይ በቅንጅት አመራሮችና በእስክንድር ነጋ መታሰር በሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ላይ ሰፊ ንግግር አድርገዋል። እኝህ ሰው ታዲያ ያላቸውን የካበተ ልምድና የ40 ዓመት የሴናተርነት አገልግሎታቸውን በመጠቀም አንቀፁ እንዲካተት በማድረጋቸው በሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በማህበረሰብ ተቋማት በኢትዮጵያውያን አክቲቪስቶችና በዲያስፖራ በሚገኙ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ምሁራን ምስጋና እየተቸራቸው ይገኛል።

የህጉ አንደምታ

ህጉ የዜጎች መብት እስካልተጣሰ ድረስ እርዳታ መሰጠቱን አይቃወምም። ድንጋጌው በሐምሌ 2013 ተጠንስሶ በቅርቡ ህግ ሆኖ የወጣው ይኸው አስገዳጅ አንቀጽ ለኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ የቤት ስራ የሰጠ ሆኗል። ተጠያቂነት አስቀምጧል። ይሄ ካልተፈፀመ እርዳታውን በቀጣይ ዓመት ማግኘት አስቸጋሪ ይሆናል።

ኢትዮጵያ ደግሞ በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ከአሜሪካ መንግስት በእርዳታ የምታገኝ በመሆኑ ይህን ርዳታ ለማግኘት ቅድመ ሁኔታዎቹን ቢያንስ በአጭር ጊዜ የማሟላት ግዴታ ይኖርበታል። እንዲህ በቀላሉ ከማንም የማታገኘው እርዳታ ስለሆነም የኢትዮጵያን መንግስት ቢያንስ የተወሰነ የፖሊሲ ማስተካከያ እርምጃ እንዲወስድ ያስገድደዋል። በቅርቡ አቶ በረከት ስምኦን እንዳሉት ገበሬው ተኛ ስንለው ይተኛል ሩጥ ስንለው ይሮጣል ምንም ብናደርገው ተሸክሞን ይዞራል ያሉት ነገር የሚሆን አልመሰለኝም።ህዝቡን እንደፈለክ በተለይ በእኛ ገንዘብ ልታሽከረክር ከአሁን በሁዋላ አትችልም እየተባለ ነውና። ያው ገበሬውም ቢሆን የሚያገኘው የእርዳታ እህል በአብዛኛው የሚገኘው ከዚቹ ከአሜሪካ አይደል? ስለዚህ ቀደም ብሎ ነበር እንጂ አሁን እንኳን የአሜሪካ መንገድ የካሮትና የዱላው አማራጭ ይመስላል።

የኦባማ አስተዳደር

የሕጉን አንቀጽ የኦባማ አስተዳደር እንዴት ሊያልፈው ቻለ? የሚለው ጉዳይ በአሁኑ ወቅት በጣም አነጋጋሪ ሆኗል። የአብዛኞቹ ምሁራን ሃሳብ ወደ አንድ ያዘነበለ ነው። እሱም አንቀጹ የተካተተው በአንድ በሺዎች በሚቆጠሩ ገፆች ባሉት የበጀት ህግ ውስጥ በመሆኑና በዴሞክራቶቹና በሪፐብሊካኖቹ መካከል በርካታ አጨቃጫቂ አንቀፆች የነበሩ በመሆናቸው ብዙ ትኩረት ሳይሰጡበት ሾልኮ አምልጧል የሚል ነው። ምክንያቱም የኦባማ አስተዳደር ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለው ጥብቅ ግንኙነት በዚህ ሁኔታ እንዲሻክር አይፈልግምና። የህጉን አንቀጽ አስተዳደሩ አውቆት ቢሆን ኖሮ ህግ ሆኖ እንዳይወጣ ያደርገው እንደነበርም መገመት ተገቢ ነው። የአሜሪካ መንግስት አቋሙ ምን እንደሆነ እስካሁን በይፋ የገለፀው ነገር የለም። ለህጉ ከመገዛት ግን ሌላ የተሻለ አማራጭ አይኖረውም። መንግስቱ ለፓርላማው ተገዥ ነውና።

የህጉ ተግባራዊነት

የህጉ ተግባራዊነት የግድ ይላል። ምክንያቱም በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አንቀጹ በህጉ ተካቶ ፀድቋል። ይህን የህግ አንቀጽ ይዘው ማንኛቸውም የኮንግረንሱ አባላት ይመለከተኛል የሚልም ዜጋና ተቋም የአሜሪካ ባለስልጣናትን ፍርድ ቤት አቁሞ ለተግባራዊነቱ ሊሞግታቸው ይችላልና።የኦባማ አስተዳደር በዚህ ሁኔታ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለው ግንኙነት እንዲሻክር ባይፈልግም የፓርላማውን ውሳኔ የማስፈፀም ሃላፊነት ስላለበት አዎንታዊ ጫና ሊያሳድር ይችላል።

የኢትዮጵያ መንግስት ምላሽ/ስጋት

በእርግጥ በጉዳዩ ላይ መንግስት እስካሁን ያለው ነገር የለም። ከነበረው ሪከርዱ መረዳት እንደሚቻለው ግን የአሜሪካ መንግስት የሚሰጠው እርዳታ አነስተኛ ነው። ከአሜሪካ የምናገኘውን እርዳታ ጨምራ ቻይና ትሰጠናለች።መንገዳቸውን ጨርቅ ያድርግላቸው። የሚሉ ምላሾች እንደሚሰጡ ይጠበቃል።

ነፍሳቸውን ይማርና የቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ የቀጥታ ስርጭት በሚተላለፍበት በአንድ የፓርላማ ስብሰባ ላይ በሶማሊያ የተካሄደውን ጦርነት አስመልክተው ስለ አሜሪካ የገንዘብ ድጋፍ ተጠይቀው አሜሪካ ኮንዶም ነው የምትረዳን በኮንዶም ነው ወይ ሶማሊያ የምንዋጋው? ብለው መናገራቸውን አስታውሳለሁ። ከዚህ በመነሳት የራዕያቸው ተረካቢዎችም ቃላት ለዋውጠው ወይ ይህንኑ ወርሰው ሊናገሩ ይችላሉ። አንዳንዶቹም አሜሪካ ሉዓላዊነታችንን ትነካለች ስለዚህ እርዳታው ይቅርብን ሊሉም ይችላሉ። የኦባማ አስተዳደርም አንቀጹ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ እንዳይሆን የመከላከል በአንዳንድ ጉዳዮችም ላይ የተለየ አቋም ሊይዝ ይችላል።

በእኔ የህግ እውቀት ከሆነ ይህ ህግ ሆኖ የጸደቀው አንቀጽ ራሱን ችሎ ያልወጣ በመሆኑና በበጀት ህጉ ውስጥ ተካቶ በመፅደቁ ብሎም ከህጉ በግልፅ መረዳት እንደሚቻለው የ2014 የዩናይትድ ስቴትስ የበጀት ህግ በመሆኑ የኦባማ አስተዳደር ካላመነበት ከአንድ ዓመት የዘለለ እድሜ ስለማይኖረው የተደረጉት ጥረቶች በድል ተጠናቀዋል /mission accomplished/ ማለት አያስችልም።

መልካም እድሎች

የኢትዮጵያ መንግስት የአሜሪካ እርዳታ ይቅርብኝ ቻይና አለችልኝ የሚል ምላሽ መስጠት አያዋጣውም። ምክንያቱም ቻይና የኢትዮጵያ መንግስት ህዝቡን ረገጠም በህዝቡ ተረገጠም ጉዳዬ ብላ አትከታተልም። ንግዷን እስካጧጧፈች ድረስ መስጠት የምትፈልገውን ትሰጣለች። ስለዚህ የአሜሪካ እርዳታ መቅረት ከፍተኛ ችግር እንደሚፈጥር በመረዳትና ወደአላስፈላጊ ግጭት እንዳይሄድ በመፍራት የኢትዮጵያ መንግስት በአፈቀላጤዎቹ/ሎቢስት ጭምር ሳይቀር ለመደራደር የሚገደድበት ሁኔታ ይፈጠር ይሆናል። ብሎም የአውሮፓ ህብረት ከአሜሪካ በላይ ለኢትዮጵያ ገንዘብ የሚረዳ ተቋም ነውና እሱም የአሜሪካ መንግስትን አቋም ደግፎ ተመሳሳይ ውሳኔ ላይ ከደረሰ የኢትዮጵያ መንግስት እጅግ ከፍተኛ አጣብቂኝ ውስጥ ነው የሚገባው። ስለዚህ ቢያንስ ቢያንስ ለፕሮፓጋንዳ እምቢኝ ዘራፍ ቢልም ቀስ በቀስ ጉዳዩን እኛም በትራንስፎርሜሽኑ እቅዳችን ይዘነው ነበር በማለት ፖሊሲዎቹን የማስተካከል እርምጃ እንደሚወስድ መገመት ይቻላል።

መደምደሚያ

ያም ሆነ ይህ ይሄ ሸንቋጭ ህግ በኮንግረንሱ ፀድቆ ወጥቷል።አሜሪካም ከመግለጫ ያለፈ እርምጃ እንድትወስድ ሲጨቀጭቋት ለነበሩት አካላት መጠነኛ እፎይታ እንዲያገኙ አድርጋለች። እሰጣ ገባው የሚወሰነው ግን በዋነኝነት የኢትዮጵያ መንግስት በሚይዘው አቋም ላይ ይሆናል።

በአሜሪካ ኮንግረንስ የፀደቀው የህግ አንቀፅ እመራዋለሁ አስተዳድረዋለሁ አገሬ ነው ዜጋዬ ነው ለሚል ስርዓት አጋዥ እንጂ ፀሩ የሚሆንበት ሁኔታ ስለማይኖር የኢትዮጵያ መንግስት የተጣለበትን ሃላፊነት ተረክቦ ለህዝቡም ለአገሪቱም የሚበጀውን ይሄን ውሳኔ ያስተግብር!አራት ነጥብ።

አዲስ አበባ የዳይመንድ ድራማ (ማጭበርበር) ተጧጡፏል!!!

ኔትዎርክ ያቆማል የተባለው የማሾ ዳይመንድ አራት ሚሊዮን ብር ተሽጧል::የዳይመንዱን ትክክለኛነት የሚያረጋግጡት የውጪ ኤክስፐርቶች ናቸው::ባለሃብቶች በሚያውቋቸው እና በቅርብ ባልንጀሮቻቸው እየተጭበረበሩ ነው::

Image

በጣም ብዙ ችግር እየደረሰብኝ ነው፡፡ አንደኛ ካገር እንድወጣ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶኛል፡፡ ሁለተኛ ከአገር የማልወጣ ከሆነ በእውነትም ይሁን በውሸት ሴራ ተጠንስሶ ወደ እስር ቤት እንደምወረወር ተነግሮኛል፡፡ ……….. እታሰራለሁ፣ እታፈናለሁና እገደላለሁ ብዬ መንግሥትና ሕግ ባለበት አገር የከተማ ውስጥ ሽፍቶችና ትናንንሽ ‹‹መንግሥት ነን›› ባዮችን ፈርቼ የማጀት አጫዋች እንደማልሆን ሊያውቁትና ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ አንዳንዶች ማንነታቸው በግልጽ ባይታወቅም፣ ዓቃቤ ሕግ በእኔ ላይ የወንጀል ድርጊት ፈልጐ ክስ እንዲመሠርት እየገፋፉት መሆኑንም ለማወቅ ችያለሁ፡፡
http://minilik-salsawi.blogspot.com/201 … st_31.html

በዜጎች ላይ የሚፈጸመው የባለስልጣናት ግፍ እና እብሪት አላባራም !!!

Image

ምንሊክ ሳልሳዊ:-በጭካኔ ፍትሕን ማምጣት እና የኢኮኖሚ አምባገነንነት ቦታ ቦታ አላቸው፡፡ ጊዜ ጊዜም አላቸው፡፡ ለመተግበር ፍፁም ጥንቃቄን ይጠይቃሉ። ውጤታቸው ጠላት ማብዛት፣ ዜጋን ማስኮረፍ፣ ሕዝብን መሬት ውስጥ መክተት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆደ – ሠፊና ለጋሥ አምባገነን መሆን የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ህብረተሰብን በቅጡ ማሳመን ይሻል፡፡ በተለይም የተለያየ ሃይማኖት፣ ባህልና ብሔረሰብ ባለበት አገር እጅግ ከባድ አስተዳደራዊ ምሉዕነትን ይጠይቃል፡፡

ኃያላን መንግሥታት ሲሻቸው የበኩር ልጅ፣ ሲሻቸው የእንጀራ ልጅ ማድረግን ይችሉበታል፡፡ ኃያላን መንግሥታት “ሲሞቅ በማንኪያ ሲቀዘቅዝ በእጅ” ገንፎ መብላትን ያውቁበታል፡፡ መልዕክተኞቻቸውን ሲሻቸው በእርዳታ ሰጪ መልክ፣ ሲሻቸው በሚሲዮናውያንና በሃይማኖተኞች መልክ፣ ሲሻቸው በዲፕሎማት መልክ፤ ካልሆነም በቀጥታ ስለላ መልክተኞች – አሊያም በቱሪስት ወይም በፒስኮር መልክ ይልካሉ፡፡ ከከፋም የውስጥ ዐርበኛ ይቀጥራሉ፡፡ ላላ ያለ ካገኙም አገራቸው ድረስ ጋብዘው፣ አስተናግደው ሾመው፣ ሸልመው አንቱ ብለው ይቀባሉ፡፡ያለ፣ የነበረ ወደፊትም የሚኖር ዘዴያቸው ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ካልተሳካ የቁርጡ ቀን መጣ ማለት ነውና እንደ ኢራቅ የጦር ዘመቻ ያካሂዳሉ፡፡ እንደግሎባላይዜሽን አበጋዞች ሳይሆን እንደጥንቶቹ ቅኝ ገዢዎች- በግልጽ ወረራ ያካሂዳሉ፡፡

ከሁሉም ይሰውረን፡፡ ሲያወድሱ ሰማይ፣ ሲጥሉ እንጦር አውርደው ከትቢያ ይደባልቃሉ፡፡ የሁልጊዜ መሳሪያቸው ነው፡፡ እስካመቸናቸው እስካልቆረቆርናቸው ድረስ ያለእኛ በትክክለኛው የዕድገት መስመር ላይ ያለ አገር አይገኝም፡፡ “እንዲህ እያልሽ ውቴልሺን ሽጪ” እንዳለው ወሎ፤ የሚነግራቸው ጠፍቶ ነው፡፡ ለእነሱ የከፋን ለታ ግን ያለእኛ ኋላቀር፣ ያለእኛ ደንቆሮ፣ ያለእኛ ጦርነት ናፋቂ፣ ያለእኛ ረሃብተኛ፣ ያለእኛ መናጢ ደሃ የለም፡፡ ”እፀድቅ ብዬ ባዝላት ተንጠልጥላ ቀረች” ይሉናል፡፡
ከበረታን፤ “አላህንም አትክዳ፣ ሐረጓንም አትልቀቅ” እንዳሉት ጠቢብ ማሰብ አለብን፡፡
የኃያላኑን የቢዝነስ ኮሙኒቲ አይተን እኛ ምን እንሥራ ማለታችን ደግ ነገር ሆኖ፤ ከእዚህ ሁሉ በስተጀርባ ምን አለ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ምን ያህል ከልባቸው ነው? እነሱ፤ ለህዝባችን ይበጃል ያሉትን ማንኛውንም እኩይ ተግባር ከመፀፈም ወደኋላ ብለው ያውቃሉን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ሁሉንም በትጋት በጉጉት – ዐይን እናስተውል፡፡

የፖለቲካ ፀሐፍት እንደሚነግሩን፤ “ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚወድቁት ስህተት ስለሚሰሩ ሳይሆን ስህተታቸውን እንዴት እንደሚያርሙ ስለማያውቁ ነው፡፡ ይሄ የእኛም ችግር ነው፡፡ ሁለት ተጠቃሽ ባህሪዎቻችን፡- “ካፈርኩ አይመልሰኝ ፣ እና “የአብዬን እከክ ወደእምዬ ልክክ ናቸው፡፡ የሠራሁት ነገር ስህተት እንዳለበት ቢነገረኝም አልለቀውም፡፡ አንዴ አድርጌያለሁ ብያለሁ፡፡ ብያለሁ፡፡ ኃያላኑም ተናግረዋል፤ ማለት አይበጅም፡፡ በተቻለ መጠን በኃያላን ውዳሴ አለመማለል ብልህነት ነው! “ቅጥ – ያጣ መረጃ” ይዘን ነው እስካሁን የሄድነው ተብሏል፡፡ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ችግሮቻችን፣ የሚጨበጡትንና የማይጨበጡትን ጨምሮ፤ ስፍር – ቁጥር የላቸውም፡፡ በአንድ የድህነት ባኮ ከትተን ልንገላገላቸው መንገድ ከጀመርን ከራርመናል፡፡ አሁንም ግን በመጨለምና በንጨላጨል መካከል ነን፡፡

በሬዲዮ ጥያቄና መልስ ፕሮግራም “የሱዳን ዋና ከተማ ማን ትባላለች” ሲባል “አማርኛ ይሁንልኝ” …“የቆጡን አወርድ ብላ…” ጨርሰው ሲባል “ስፖርት ይሁንልኝ”፤ ዓይነት መልስ የሚመልስ ህብረተሰብ ይዘን እየዳከርን ነው፡፡ አገራችን፤ ላዩም ታቹም ይሄን መሳይ ነው!ሰማይ ሰማይ ስናይ እግራችን ሥር ያለውን ነገር አንዘንጋ፡፡ ሰማዩን አተኩረን ስናይ ቀልባችን ሙሉ በሙሉ እሱ ላይ ብቻ ካረፈ፤ ከሥር እግራችንን የሚመታንን እንቅፋትና የሚያሰምጠንን ጉድጓድ አናየውም፡፡ ወደኃያላን መንግሥታት ስናንጋጥጥ የራሳችንን ህዝብ እንረሳለን፡፡ አልፈን ተርፈንም የሰዎችን ዕጣ-ፈንታ ስንናገር የራሳችንን ዕጣ-ፈንታ ሳናቅ እንዳንቀር እንጠንቀቅ!

Image

የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት የነበሩትና ከሃላፊነታቸው በግምገማ ከተነሱ በኋላ የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን ተሹመው የነበሩት አቶ ኡሙት ኡባንግ ከአገር መኮብለላቸው ታውቋል፡፡

ከሳምንት በፊት ለሚሰሩበት የሚኒስትር መስሪያ ቤት ሳያሳውቁ ከአገር ስለመውጣታቸው የተነገረባቸው አቶ ኡሙት ኡባንግ ለቅርብ ሰዎቻቸው ወደ አገር የመመለስ ፍላጎት እንደሌላቸው መናገራቸውን አዲስ አድማስ ጋዜጣ አስፍሯል፡፡

የሚኒስትር ዲኤታውን ኩብለላ በተመለከተ በአዲስ አድማስ የተጠየቁት የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም ፣አቶ ኡመድ በስራ ገበታቸው ላይ እንደሌሉ ማረጋገጣቸውን ገልጸው መስሪያ ቤታቸው ጉዳዮን እያጣራ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

የትግራይን ሕዝብ ከብሄር ጭቆና ነጻ አወጣለሁ በሚል ጠባብ ዓላማ ተደራጅቶና ታጥቆ ለበትረ ሥልጣን የበቃው ህወሃት ወይም ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሥልጣን ከተቆጣጠረ 23 አመት ሊሞላው እነሆ ጥቂት ወራቶች ብቻ ቀርተውታል።
ለጋራ ቤታችን ለሆነቺው አገራችን ኢትዮጵያና በአስተዳደር በደል ለከፋ ድህነት ለተዳረገው መላው ሕዝቦቿ የሚሆን አንዳችም ራዕይ ሳይኖረው ለመንግሥትነት ሥልጣን የበቃው ይህ ቡድን ላለፉት 23 ዓመታት ከግል ኑሮአቸው አሻግረው የአገርንና የወገንን ጥቅም ማየት የማይችሉ ወይም የማይፈልጉትን በዙሪያው አሰባስቦ እያካሄደ ካለው ዘርፈ ብዙ የሃብት ምዝበራ ወንጀል በተጨማሪ እየፈጸመ ያለው የመብት ጥሰትና አፈና ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም።

ሰሞኑን እያፈተለኩ በመውጣት ላይ ከሚገኙ ምስጥራዊ የድምጽ መረጃዎች ለማረጋገጥ እንደተቻለው ደግሞ ለጥቂቶች የሃብትና የብልጽግና ምንጭ የሆነው ሥልጣን ከእጃቸው እንዳይወጣ በአንድ በኩል በምርጫ ስም እንዴት አድርገው ሕዝቡን ቀፍድደው የምርጫው ተሳታፊ ማድረግ እንደሚችሉ ሲዶልቱና በሌላ በኩል ደግሞ በቁጥጥራቸው ሥር የሌሉትንና ለሥልጣናቸው ያሰጉናል ያሉዋቸውን የደሃዉን ልጅ በማጋፈጥ እንዴት በጦርነት እንደሚጨፈልቁዋቸው ሲመክሩ ተሰምተዋል።

ከወያኔው ቁንጮ አንዱ የሆነው በረከት ስሞን በየደረጃው ላሉት የአገዛዙ ሹሞችና ካድሬዎች ባደረገው ገለፃ መሬትን የመንግሥት ባደረገው ኮሚኒስታዊ አዋጅ ምክንያት የመንግሥት ጭሰኛ ለመሆን የተፈረደበትን ሰፊውን አርሶ አደር “ተኛ ስንለው ይተኛል፤ ቁም ስንለው ይቆማል ፤ እንደፈለግን ብንበድለው እንኳ አያማርረንም ” እያለ ሲዘባበትበት ተደምጦአል ። በአንድ ለአምስት ኮሚንስታዊ አደረጃጀት ተጠርንፎ የወያኔ የንግድ ድርጅቶች ብቻ የሚያቀርቡትን ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ያለውዴታው እንዲራገፍበትና ከአቅሙ በላይ ዕዳ እንዲቀፈቅፍ የተፈረደበት የኢትዮጵያ አርሶ አደር በዚህ አይነት ንቀት ደረጃ የሚዘባበትበትን መሪ ከወያኔው በረከት ስሞን በፊት ገጥሞት አያውቅም ። ለወደፊትም ሊያይ አይፈልግም ። ወያኔን ሥልጣን ላይ ለማምጣት የሰሜኑ ክፍለአገራችን አርሶ አደር የተጫወተው ሚና ተዘንግቶ በበረከት ስሞን እንዲህ መዋረዱ እጅግ ያሳዝናል። ለነገሩ ከፍተኛ የህይወት መስዋዕትነት ከፍሎ ለድል ያበቃው የትግራይ ሕዝብ ቁም ስቅሉን እያየ አይደል?

ሌላው አስገራሚ ክስተት በአገር ደህንነት ሥራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች ባደረጉት ዝግ ስብሰባ ታማኝነታችን ለአገራችን ነው ወይስ የሥርዓቱን አገዛዝ ዕድሜ ለማራዘም? ብለው ላነሱት ጥያቄ የጠቅላይ ሚንስትር ተብዬው የህግ አማካሪ ጌታቸው ረዳ የሰጠው መልስ ነው። ደህንነት ብቻ ሳይሆን የመከላኪያ ሠራዊትና ፖሊስ ጭማር ታማኝነታቸውና ግዴታቸው ሥርዓቱን ሥልጣን ላይ ማቆየት መሆን አለበት ሲል ጌታቸው እንቅቹን ነግሮአቸዋል ። በምላሹ “ላለፉት 23 አመታት እያደረግነው ያለው ይሄው ሆኖ ሳለ አሁን ምን ብታስቡ ነው ጥያቄ ያነሳችሁ?” የሚል ይመስላል ። ይባስ ብሎም ሥርአቱን ለመጠበቅ ያልቻለና በግንቦት 7 መንገድ የሚጓዝ ደህንነት ሠራተኛ የተስፋየ ገብረስላሴን ያህል የደህንነት እውቀት ቢኖረውም ሆነ እስራኤል አገር የዓመታት ስልጠና ያገኘ ቢሆን ዋጋ የለውም ብሏቸዋል።
ለመሆኑ ወያኔዎች እንደመርገም የቆጠሩትና ተከታዮቻቸውን የሚያስፈራሩበት የግንቦት 7 መንገድ ምንድ ነው።?

ግንቦት 7 የፍትህና፤ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አገራችን ኢትዮጵያ የእያንዳንዱ ዜጋ ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብት የተከበረባት፤ የኢኮኖሚ ብልፅግናና ማኅበራዊ ፍትህ የሰፈነባት ፤ የዜጎች ሕይወት፣ ደህንነትና ጥቅም የተከበረባት እና የሕዝቧ አንድነትና ትስስር የጠነከረባት ሃገር ሆና ማየትን ብቸኛ ራዕይ አድርጎ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ ድርጅት ነው። ይህንን ራዕይ እውን ለማድረግ ደግሞ እስከ ዛሬ በጠመንጃ ኃይልና በጉልበተኖች ጡንቻ ከአንዱ ወደሌላው የሚፈራረቀው የመንግሥት ና የፖለቲካ ሥልጣን በሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ሂደት የሚያዝበትን ፤ የሃገሪቱ ዜጎች ምርጫ በተግባር የሚገለፅበት፤ ማኅበራዊና የፖለቲካ ችግሮች በዲሞክራሲያዊ መንገድ የሚፈቱበት እና ዲሞክራሲያዊ ባህል የሚበለፅግበት ብሄራዊ የፖለቲካዊ ሥርዓት መገንባት አማራጭ የሌለው ነው ብሎ ያምናል።
ይህ ደግሞ ያለምክንያት አይደለም። ወያኔ የዓለም አቀፍ ድጋፍ ለማግኘት ሲል ለዲሞክራሲያዊ ምርጫ በሩን ከፈት አድርጎ በነበረበት ምርጫ 97 ወቅት ከተገኘው ልምድና ከተመዘገበው ውጤት ሕዝባችን በአምባገነኖችና በከፋፋዮች ለመገዛት አለመፈለጉን በግልጽ አስመስክሮአል።

ንቅናቄያችን ግንቦት 7 ሕዝባችን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በነቂስ ወጥቶ መሪዎቹን የመረጠበትንና ድሉን የተነጠቀመበትን ታሪካዊ የግንቦት 7 1997ን ቀን ምን ጊዜም አይረሳም። መጠሪያ ስሙንም በዚያ ታሪካዊ ቀን የሰየመው ሕዝብ የተነጠቀውን ድል በማስመለስ ፍትህ የሰፈነባት፤ የበለጸገችና የተከበረች አገር ባለቤት እንሆን ዘንድ ነው። ሁላችንም አትራፊ እንጂ ተጎጂ ለማንሆንበት ለዚህ ቅን አለማና ራዕይ ደንቃራ ሆኖ የተገኘው ወያኔና ለግል ጥቅማቸው ሲሉ ከወያኔ ጋር የተጣበቁ አንዳንድ ባዕዳን አገሮች ናቸው።
ወያኔ የግንቦት 7 መንገድ የሚለው ለዚህ ክቡር ዓላማ ሲባል እንቅፋት የሆነውን ሥርዓቱን በሁለ- ገብ ትግል አስገድዶ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር አካል ማድረግ ካልተቻለ ደግሞ በተባበረ ትግል አስወግዶ በምትኩ በሕዝብ ለሕዝብ ከሕዝብ የሚመጣ ሰላማዊ የመንግሥት ሥርዓት መመሥረትን ነው። ይህንን የተቀደስ አላማ ለማክሸፍና የተጀመረውን ትግል ለመጨፍለቅ ሲባልም ወደ ሥልጣን ለመምጣት በጦርነት ማግዶ ካስጨረሳቸው የደሃ ልጆች በእጥፍ የሚበልጡትን መልምሎ በጸረ ሽምቅ ውጊያ ከማሰልጠን ጎን ለጎን ለግንባታ ቢውል ስንት ፋይዳ ሊያስገኝ ይችል የነበረ በርካታ ገንዘብ በማፍሰስ ተቃዋሚ ድርጅቶችን ድምጽ ለማፈንና ለመሰለል እየተንቀሳቀሰ ይገኛል።
ለአገራችን ሉአላዊነት ጠቀሜታው እስከዛሬ ምንም ባልታወቀ ጦርነት ወደ መቶ ሺ የሚጠጉትን ያስጨፈጨፈ፤ የተልዕኮ ጦርነት ለማካሄድ በመንግሥት አልባዋ ጎረቤት ሱማሌ እስከዛሬ ቁጥራቸው ያልተገለጸ ወገን ያስፈጀ ፤ ለሥራ ፍለጋ ውትድርና የገቡትን ወጣቶች ለይቶ በሰላም አስከባሪ ስም በድንበር ዘለል ጦርነቶች እየማገደ ገንዘብ የሚቀበል፤ ስለአገርና ስለወገን ምን ሊገደው ይችላል?
ትናንት ትግል ላይ በነበሩበት ወቅት የቀደምቶቹ መንግስታት ልጆቻቸውን ለትምህረት ወደ ፈረንጅ አገር እየላኩ የደሃውን ልጅ በጦርነት ይማግዳሉ በማለት በጅምላ ሲከስ የኖረ ዛሬ በተራቸው ልጆቻቸውን ብቻ ሳይሆን ዘርማንዘሮቻቸውን ታይቶ በማይታወቅ ብዛት ወደ ፈረንጅ አገር ለትምህርት እየላኩ ለነጻነታችንና ለክብራችን የምንታገለውን እርስ በርስ ለማጨራረስ ሲዶልቱ ዝም ብሎ መመልከት ከየትኛውም ቅን ዜጋ የሚጠበቅ አይሆንም።
ስለሆነም የበላይ አዛዦቻቸው በሚሰርቁት የሕዝብ ገንዘብ ፎቅ ላይ ፎቅ እየገነቡ ሃብት በሚያካብቱት አገር ሠራዊቱን እረፍት ለመንሳት ሆን ተብለው በሚቀሰቂሱት ግጭቶች ከአንዱ ማዕዘን ወደ ሌላው ማዕዘን ያለ ዕረፍት እየተንከራተተ ያለው የመከላኪያ ሠራዊት ፤ የፖሊስና የደህንነት ኃይል ለአገዛዙ አልታዘዝም በማለት ተገዶ ሥልጣን ለሕዝብ እንዲያስረክብ የማድረግ ወገናዊ ሃላፊነቱን እንዲወጣ ግንቦት 7 የፍትህ የነትጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ጥሪውን ያቀርባል።
የግንቦት 7 መንገድ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዘመናት የተጠማውን ፍትህ እኩልነትና ነጻነት በአገራችን ለማስፈን አሁን ሥልጣን ላይ ያለው የጎጠኞችና የዘራፊዎች ስብስብ በማስገደድ ወይም በማስወገድ ሰላማዊ ህጋዊና ዲሞክራሲያዊ የሥልጣን ሽግግር እንዲኖር ማድረግ ነው። ይህንን ደግሞ የሚፈሩት በሥልጣን ቱርፋትና በሃብት ዘረፋ የሰከሩ ብቻ ናቸው።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ

የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር የአገራችን ኢትዮጵያን ዳር ድንባር ለሱዳን ለማስረከብ ሽር ጉድ እያለ የሚገኘውን የወያኔን አገዛዝ ጸረ-አገርና ጸረ-ህዝብ እንቅስቃሴ በመቃወም በመተማ አካባቢ ልዩ ስሙ ዘባጭ ባህር በተባለ ቦታ ከወያኔው 24ኛ ክፍለ- ጦር ጋር በጥር 21- 2006 ዓ.ም ከቀኑ 6 ሠዓት ላይ ባደረገው ውጊያ 14(አስራ አራት) ገድሎ 12(አስራ ሁለት) አቁስሏል።

በመተማና አካባቢው በተደጋጋሚ በአርበኛው ጥቃት እየተፈፀመበት የሚገኘው የወያኔው ቅጥረኛ ሠራዊት ህይወቱን ለማትረፍ እግሩ ወደመራው እየፈረጠጠ መሆኑ ሲታወቅ በደረሰበትም ጉዳት ማካካሻ ይሆነው ዘንድ ሰላማዊውን ነዋሪ በእናንተ ምሽግነት ነው እየተመታን ያለነው በሚል እንግልት እያደረሱበት መሆኑ ታውቋል።

በተያያዘ ዜና በጭልጋ ወረዳ ጫቁ የተባለ አካባቢ ነዋሪዎች ከብት፣በግና ፍየል በአካባቢው የወያኔ ታጣቂዎች እየታረደ እየተበላባቸው መሆኑ ታውቋል።

በዚሁ አካባቢና አጎራባች ወረዳዎች የወያኔው ተላላኪዎች ተደጋጋሚ ንብረትን የመዝረፍ ሂደት የተቆጣው ነዋሪ ለምንድን ነው ንብረታችንን የምትዘረፉት ምን አደረግናችሁ ብለው ሲጠይቁ እናንተ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ደጋፊዎች ፣መንገድ መሪዎች እንዲሁም ስንቅ አቀባዮች ናችሁ የሚል ምክንያት የሰጧቸው መሆኑ ታውቋል።

በጎንደር ክ/ሃገር ሳንጃ ወረዳና አካባቢው ሕዝብን ሲያሰቃይ ነበሩ የተባለት የልዩ ሃይል አዛዥ ሻለቃ ቀለሙ ክብረት መገደሉ የአርበኞች ግንባር ለግድያው ሃላፊነቱን ወስዶ “ግለሰቡ የተገደለው በጥር 21-2006 ዓ.ም ከቀኑ 12 ሰዓት ላይ በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰርጎ ገቦች ማሰሮ ደንብ የተባለ ቦታ በጥይት ተደብድቦ ቆስሎ ወዲያውኑ ወደ ጎንደር ቸቸላ ሆስፒታል ቢወሰድም በማግስቱ ማለትም በጥር 22-2006 ዓ,ም ህይወቱ አልፏል።” ብሏል።

እንደ አርበኞች ግንባር ገለጻ ከሆነ “ይህ ግለሰብ በወረዳው የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችን የአርበኞች ደጋፊ ናችሁ በሚል ሲያሰቃይ የነበረ ሲሆን፣ ብዙ ንፁሃን ግለሰቦችን በድርጅቱ ደጋፊነት ስም እየፈረጀ እንደገደለ፣ እንዳሰረና እንዲሰደዱ ሲያደርግ የነበረ መሆኑ ይታወቃል ። ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ግለሰቡ ከድርጊቱ ታቅቦ ሰላማዊ ኑሮውን እንዲኖር ካልሆነ ግን አስፈላጊው እርምጃ እንደሚወሰድበት የፅሁፍ መልዕክት የደረሰው ቢሆንም ሊታረም ባለመቻሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰርጎ ገቦች እርምጃ እንዲወስዱበት ተደርጓል።” ብሏል።

“በጎንደር አካባቢ ምንም አይነት ወታደራዊ እርምጃ በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሠራዊት ሲወሰድ የአካባቢውን ሕዝብ ማንገላታቱ የተለመደ ቢሆንም ሻለቃ ቀለሙ ክብረት ከሞተበት ከትናንት ጀምሮ ግን በህዝቡ ከፍተኛ ስቃይ እያደረሰበትና ገዳዮቹን ታውቃላችሁ እናንተ ናችሁ እየደበቃችሁና ቀለብ እየሰፈራችሁ የምታስጨርሱን በሚል ብዙ ሰዎች እንደታሰሩ ታውቋል።” የሚለው የአርበኞች ግንባር ዜና “የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ወታደራዊ መምሪያ በበኩሉ ወደፊትም ቢሆን ወያኔና ተላላኪዎቹን ከዚህም በከፋ ሁኔታ አይቀጡ ቅጣት እንደሚቀጣ አስታውቆ ሕዝቡም ከመሬቱና ከንብረቱ እየተፈናቀለ መኖሩ ያበቃ ዘንድ ከኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት ጎን በመሰለፍ ይህን አፋኝ ስርዓት ለመገርሰስ የበኩሉን አስተዋፅዖ ማበርከት እንዳለበት ጥሪያችንን እናስተላልፋለን” ብሏል።
http://www.arbegnochginbar.org/

የዓረና ትግራይ 3ኛ ድርጅታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔዎች ተግባራዊ ለማድረግ በትግራይ ከተሞች ተከታታይ የህዝብ ፖለቲካዊ ስብሰባዎች በማካሄድ በክልሉ ያንሰራፋው ብልሹ ኣስተዳደር ምንጩና መፍትሄው፣ የዓረና ትግራይ ፓርቲ የፖለቲካ ራኢና ኣማራጭ ያንሰራፋው ብልሹ ኣስተዳደር የማስቀረት ብቃት ለማሣየት አስመልክቶ ከህዝብ ለመምከርና በትግራይ ከተሞች ህዝባዊ ፖለቲካዊ ስብሰባዎች ለማካሄድ እቅድ ተይዞ ከመጀመርያው የጥቅምት ወር 2006 ዓ/ም ጀምሮ በተከታታይ ለማካሄድ እንቅስቃሴ ተጀመረ። ህዝባዊ ፖለቲካዊ ስብሰባው በቅደም ተከተላቸው በውቕሮ፣ በማይጨው፣ በዓብይ ዓዲ ከተሞች ህዝባዊ ፖለቲካዊ ስብሰባዎች ሲካሄዱ ህዝብ ወደ ስብሰባው እንዳይመጣ የማደናቀፍ ተግባር በገዢ ፓርቲው የአከባቢ ካድሬዎች የታየ ቢሆንም ህዝቡ የማዳመጥ ፣አስተያየት የመስጠት መብቱን ለመጠቀም ባሳየው ፍላጎት በስብሰባው አዳራሽ በመገኘቱ ውጤታማ የህዝብ ስብሰባዎች ማካሄድ የተቻለ ሲሆን በሽረ ከተማ የህዝብ ስብሰባ ለማካሄድ ህዝቡ ወደ ስብሰባ ኣዳራሽ እንዲመጣ በሚገባ ከተቀሰቀሰ ህዝቡም ጥሪውን ኣክብሮ ወደ ኣዳራሹ በጥዋቱ እንደመጣ የከተማው ኣስተዳደርና በፓርቲው መዋቅር በተደራጀ ረብሻ የህዝብ ስብሰባው ሳይካሄድ መቅረቱን ይታወሳል፡፡ በዕቅዱ መሰረት ፓርቲያችን በምስራቃዊ ዞን ዋና በዓዲግራት ከተማ ጥር 18 ቀን 2006 ዓ/ም የህዝብ ፖለቲካዊ ስብሰባ ለማካሄድ ኣዳራሽ እንዲሰጠን ለከተማው ኣስተዳደር ተጠይቆ ኣዳራሽ ተይዞኧል ኣይቻልም የሚል መልስ በመስጠታቸው እንግዲያው ስብሰባው በኣደባባይ እናደርገዋለን ሲባሉ ተመልሰው ኣዳራሽ ተፈቅዶላችኃል የሚል ምላሽ ተስጥቶን በስብሰባው ቀን ህዝቡ ተገኝቶ ዓረና ባዘጋጀው ኣጀንዳ እንዲመክር ለማስቻል የዓረና ከፍተኛ ወጣት ኣመራሮችና ኣባሎች በዓዲግራት ከተማና ኣከባቢዋ ተሰማርተው በሕገ መንግስቱ የተረጋገጡ ሃሳብነ በነፃ የመግለፅና የፖለቲካ ፓርቲዎች የመንቀሳቀሰ ነፃነት የሚያረጋግጡ መብቶች በመጠቀም በህዝባዊ ስብሰባው የሚመክርባቸው ኣጀንዳዎችና የስብሰባው ቀን፣ ስዓትና ቦታ የሚገልፀው ፅሑፍ በማደል ተሰማርተዋል፡፡
ለህዝቡ የሚታደለው ፅሑፍ የሚፈነዳ ቦንብ ኣልነበረም ወደ ህዝቡ ህሊና ዘልቆ የሚገባ ሓሳብ ብቻ ነበር፡፡ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ዓረና ትግራይ የመሬት ባለቤትነት የመንግስት መሆኑ ቀርቶ የህዝብ/ዜጎች እንዲሆን የመሬት ሊዝ ኣዋጅ እንዲሻር፣ ዜጎች ለመኖርያ የሚስፈልጋቸው ቦታ በሕገ መንግስቱ መሰረት ያለ ሊዝ የማግኘት መብታቸው እንደሚረጋገጥ፣ ለወጣት ሴቶችና ወንዶች በግፍ ለስደት መዳረግ ምክንያት የሆነው ብልሹ ኣስተዳደር በማስወገድ በሃገራቸው ሥራ የማግኘት መብታቸው እንደሚረጋገጥ፣ የሙያ ብቃት መስፈርት መሰረት ባደረገ መርህና የሙያና የኣካዳሚ ነፃነት በማረጋገጥ የመመህራንና የመንግስት ሠራተኞች ችግር ለማስወገድ እንደምንሰራ፣ በኣስገዳጅ የማዳበርያ ግዢ ለገዢው ፓርቲ የንግድ ድርጅቶች ብዝበዛ የተጋለጡና በእዳ ተጭነው ለጎስቋላ ኑሮ የተዳረጉት የትግራይ ገበሬዎች ችግር ለማስወገድ የማደባርያ ግዢ በውዴታ እንደሚሆንና ግብርናውና ገበሬው ለመደገፍ ለገበሬው ድጎማ ማድረግ እንደማያስፈልግ፣ ትምህርት ቤቶች ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ነፃ እንደሚሆኑ ዋና ስራቸው የፓርቲ ኣባል ምልመላና በትምህርት ቤቶች ለሚነሱ የመብት ጥያቂዎች ማኮላሸት የሆነ የህ.ወ.ሓ.ት (ኢህኣደግ) የ 1-5 የትምህርት ኔትወርክ እንደሚቀር፣ በትግራይ ህዝብ ደምና ኣጥንት የተገኘው ሙሉ በሙሉ የትግራይ ህዝብ ሃብትና ንብረት የሆነው ት.እ.ም.ት ከህወሓት መንጋጋ ኣውጥቶ ተጠሪነቱ ለክልሉ መንግስት በሆነ በነፃ የባለሙያ ቦርድ እንዲተዳደር በማድረግ የክልሉን ማሕበራዊ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት እነዲውል የማደረግ መሆኑ፣ በት.እ.ም.ት ሥር የሚተዳደሩ የልማት ድርጅቶች ሠርተው የሚያገኙት ትርፍ በትግሉ ለተጎዱ ታጋዮችና ሲቭል ኣርበኞች እንዲሁ የሻዕብያን ወራራ ለመመከትና ሃገራቸውን ለመጠበቅ ለጉዳት የተዳረጉ ኣርበኞችና ቤተሰባቸውን ለመደገፍ እንደሚውል፣በሕገ-መንግስቱ እንደተደነገገው ገዢው ፓርቲ በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት እንዲያቆም የሚጠይቁ ነበሩ፡፡ እነዚህ የአማራጭ ፖለቲካዊ ፕሮግራም ኣጀንዳዎች ሙሉ በሙሉ ሓሰቦች እንጂ የሚፈነዱ ፈንጂዎች ኣልነበሩም ! እነዚህ በጠራራው ፀሃይ ለህዝቡና ለህ.ወ.ሓ.ት ኣባላትና ደጋፊዎች ጭምር የቀረቡ ኣጀንዳዎች ነበሩ፡፡
እነዚህ ለህዝቡ የቀረቡ የአማራጭ ፖሊሲ ኣጀንዳዎች በሳዕሲዕ ፃዕዳ እንባ ወረዳ ዋና ከተማ ዕዳጋ ሓሙስ ለህዝቡ ሲታደሉ አንዲት ወረቀት ሳትቀደድ ኣንድ ሰው እንኳን ኣልቀበልም ሳይል ሁሉም በደስታ ተቀብሎ ለወጣት ኣመራሮቹ በኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ሙሩቕና የዓረና የሥራ ኣስፈፃሚ ኣባልና የህዝብ ግንኙነት ሓላፊ ኣቶ ዓምዶም ገ/ስላሴና መም/ ሃይለ ገብረፃዲቕ ያሳየው አክብሮት የሚደነቅ እንደነበረ ይመሰክሩለታል፡፡ በሻዕብያ የወደመችው የጎሎመኸዳ ወረዳ ዋና ከተማ የነበረችው ውብዋ ዛላንበሳን በመተካት የከተመችው የፋፃ ከተማ ነዋሪዎችና የኣካባቢው ገበሬዎች የስብሰባው ኣጀንዳ፣ ጊዜና ቦታ የሚገልፀው ፅሑፍ ሲታደላቸው ህዝቡ በሰላም ተቀብሎ እንዳስተናገዳቸው ” ቀድመን መመጣታችሁ ብናውቅ ኖሮ ሻይ ቁርስ ኣዘጋጅተን እነቆይ ነበር” በማለት በኣክብሮት እንደተቀበላቸው በኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ምሩቅና የዓረና ትግራይ የድርጅት ጉዳይና የፅሕፈት ቤት ሓላፊ የሆኑት ኣቶ ስልጣኑ ሕሸ ና ኣቶ ሃይለኪሮስ ተፈሪ የህዝቡ ጨዋነት እንግዳ ተቀባይነትና ለኣማራጭ ሓሳብ ያለው ጥማት ይመሰክሩለታል፡፡ የዓዲግራት ከተማ ህዝብ ኣቀባበልም ተመሣሣይ ነበር፡፡
የህዝቡን የልብ ትርታ ያለማራቸው የዘኑ የገዢው ፓርቲ ኣስተዳዳሪዎች ዓረናና ህዝቡ የማይገናኙበት፣ የህዝቡ ስብሰባ የማካሄድበትና የዓረና ወጣት ኣመራሮች ሞራላቸው ተጎድቶ የሚያርፍበት እኩይ ብልሃት መዘየድ ጀመሩ፡፡ በዕዳጋ ሓሙስ የህ.ወ.ሓ.ት መታወቅያቸውን በማሣየት ለህዝቡ የስብሰባ ጥሪ የሚያድሉ የዓረና ኣባላትን ማቆም ጀመሩ፤ በፓርቲ መታወቅያ የመንግስት ሥራ መስራት ኣትችሉም ሲባሉ ሁሉም በእጃቸው ሁሉም በደጃቸው የሆነላቸው የህወሓት አባላቱ ወድያው ፖሊስ ጠርተው የዓረና ኣባላትን ኣቶ ዓምዶም ገ/ስላሴንና መም/ሃይለ ገ/ፃድቅን ወደ ፖሊስ ጣብያ በእስር ወሰዱ፡፡ አባላቶቻችን መታወቅያቸውን እንዲያሳዩ ተጠየቁ ኣሳዩ፡፡ (1) መመ/ሃይለ ገ/ፃድቅ የዓረና መታወቅያ ስለሌህ የዓረና ፅሑፍ ማደል ኣትችልም ተባለ (2) የሚታደሉት ፅሑፍ የዓረና ማህተም ስለሌለው ለህዝብ መሰጠት ኣትችሉም ተባሉ (3) ፅሑፍ እያደላችሁ የመኪና መንገድ ትዘጋላችሁ ኣሉ የህወሓት ካድሬዎቹ በድፍረት !? በስንት ንትርክ ለሚያጋጥማቹሁ አደጋ በራሳችሁ ሓላፊነት ተብለው ሥራቸውን ቀጠሉ፡፡ በራሳችሁ ሓላፊነት? ሲባል ብትደበደቡ ብትዋረዱ ብትገደሉ የሕግ ከላላ ኣንሰጥም ማለት ነበር፡፡ ያለምንም እንከን ህዝቡ በሰጣቸው ሞራል ስራቸውን በሚገባ ፈፅመው በደስታ ወደ ዓዲግራት ተመለሱ። ይህ የሆነው ዕለት ሓሙስ ጥር 15 ቀን 2006 ዓ/ም ነበር፡፡ በዓዲግራት ኣቶ ኣስገደ ገ/ስላሴና ኣቶ ኣብርሃ ደስታ እንዲሁም መም/ፍፁም ግሩምና መመ/ገዛኢ ንጉሰ ኢሉ፡፡ ሓሙስ ጥር 15 ቀን 2006 ዓ/ም የስብሰባ ጥሪ የሚገልፀው ፅሑፍ በዓዲግራት ማደል ማደል ተጀምረዋል፡፡ ዕለተ ዓርብ ጥር 16 ቀን 2006 ዓ/ም የዓዲግራት ከተማ ሰፊ በመሆኑ ኣቶ ስልጣኑ ሕሸ፣ ኣቶ ሃይለኪሮስ፣ መም/ገዛኢ ንጉሰ፣ መመ/ፍፁም ግሩም በቀበሌ 01 ሲንቀሳቀሱ ህዝቡ ምግብና ውሃ እየሰጠ የስብሰባው ጥሪ እየተቀበለ በክብር እንዳስተናገዳቸው ይመሰክራሉ።
ይህንኑ እውነት እየተከታተሉ ይታዘቡ የነበሩ የጥፋት መልእክተኞች የዓረና መመራርና ኣባላት ለማወክ ተዘጋጅተው ኖረው የስብሰባው ጥሪ ለህዝቡ የሚያድሉ ወደ ሆስፒታል ኣከባቢ ሲደርሱ የቀበሌ ካድረ የሆኑ ሴቶች ወረቀቱን ተቀብለው መቅደድ ጀመሩ፡፡ ዕድሜኣቸው ከ12-16 ዓመት እንደሆኑ የሚገመቱ ህፃናትም መሰብሰብ ጀመሩ ሆ! እያሉ መረበሽ ጀመሩ፣ ሴቶቹ መብታቸው በማለት አደፋፈሩ። የማወክ መብት? ህፃናቱ የተላኩ እንጂ የራሳቸው ኣጀንዳ የሌላቸው መሆኑ በተግባር ለመፈተን የወዳደቁ የስኳርና የቡና መጠቃለያ የደብተርና የጋዜጣ ፅሑፎች ሲሰጣቸው የዓረና ፅሑፍ መስሎአቸው ሳያዩት ተቀብለው ወድያው ይቀዱታል ልክ የስብሰባው መጥሪያ ፅሑፍ ተቀብለው እንደቀደዱት፡፡ ለህፃናቱ መብታችሁ ነው እያሉ የሚያጅቡ ትላልቅ ወንዶችና ሴቶችም ነበሩበት ። ህፃናቱ ሁሉም ሊባል በሚችል ሲጋራ ያጤሳሉ ፣ ስትቀርባቸው መጠጥ መውሰዳቸው የሚሳውቅባቸው በእጅጉ ጠጅ ይሸቱ ነበር። የአከባቢው ሰዎች በሰጡት መረጃ መሰረት የተለያየ ሱስ ተጠቃሚዎች ለመሆናቸው በከተማው ፖሊስ የሚታወቁ ናቸው።በዚህ የውንብድና ተግባር በዓረና ከፍተኛ ወጣት አመራሮችና አባሎች የአካልና የሞራል ጉዳት ተፈፅሞአል ፣ የቀበሌ ሴቶች በፌስታል አፈር እያቀበሉ ህፃናቱ በአዓረና አባላት በላያቸው ላይ አፈር በማፍሰስና እክታ በመትፋት አሳፋሪ ወንጀል ሲፈፀም በዓዲግራት ከተማ የሚገኙት የከተማው አስተዳደርና ፖሊስ የዞኑ አስተዳደርና ፖሊስ መብታቸው ነው እያሉ ያሳዩት የወንጀል መተባበር አሳፈፋሪ ተግባርና መንግስታዊ ውንብድና የሚያሰኝ ነው።
በዛው ጨዋ ህዝብ ፊት እነደዚህ ያለ የውንብድና ተግባር ተፈፀመ፡፡ ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው ተግባሩ የተቀነባበረው በዞኑ በከተማው መስተዳድር ስለመሆኑ ኣስተዳዳሪዎች፣ ፖሊስ ያሳዩት ተግባራቸው ይመሰክርላቸዋል፡፡
በነዚህ ጥቂት ቀናት የዞኑ መስተዳድር የፀጥታ ኣደጋነቱን በተግባር ሲያስመሰክር ህዝቡ ደግሞ የሕግ ኣስከባሪነት ሚናው መወጣቱን በገሃዱ ዓለም ቁጭ ብሎ ታይቶኣል፡፡ መስተዳደሩ በራሳችሁ ሃላፊነት የህግ ከለላ ኣንሰጣችሁም ሲል በዓረና ኣመራሮችና ኣባላቶች ሊያወርዱት የከጅሉት ወንጀል ጠቋሚ ነበር። የህዝብ ስብሰባው እንዳይካሄድ የተፈጠረው ውንብድና የመስተዳድሩ እጅ እንዳለበት የሚያሳየው –
የዞኑና የከተማው መስተዳደርና ፖሊሲ በኣባሎቻችን የተፈፀመውን በዓይናቸው ያዩት ወንጀል ማጠራትና ማስቆም ሲገባቸው ፍርደ ገምድል እንዲሉ በሞባይል ስልክና፣በካሜራ ቀርፃችሁናል ህፃናቱም ቀርፃችሁኣል ትፈተሻላችሁ ብለው የሁሉም አባሎቻችን ሞቫይልና ካሜራ ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ መቦርበራቸው፣
በተደራጀና በህፃናት ከለላ የተደበቀ የወንብድና ተግባር ሲፈፀም መስተዳደሩና ፖሊሱ እያዩ በጠራራ ፀሃይ በኣባላቶቻችን ላይ ኣሰቃቂ ግፍ እነዲፈፅሙ ሙሉ ፍቃድ ማሳየታቸው የሚያስቆጥራቸው በመሆኑ ፣
በሕግ የተቋቋመ ፓርቲ የቆመለትን ራኢና ፖሊሲ ለህዝቡ ለማስተዋወቅና በክልሉ ያንሰራፋው ብልሹ ኣስተዳደር የሚገራበት መንገድ ከህዝቡ ለመምከር ያደረግነው ጥሪ እንዳይሳካ ለማወክ የተላኩ ህፃናት መብታቸው ነው እያሉ የሕገ-ወጥ ተግባር ከለላ መስጠታቸውና ለባሰ ጥፋት እንዲዘጋጁ ማበረታታቸው የወንጀሉ ተሳታፊ የሚያደርጋቸው መሆኑን
የከተማ ፖሊስ የኣረና ኣባላት ባረፉበት ሆቴል ማታ አልጋ በያዙበት ሆቴል ከምሽቱ 4፣00 ሰዓት ተገኝቶ እሁድ ለሚካሄደው ስብሰባ የእግር ኳስ፣ የብስከሌታ ውድድር ስላለ በቂ የፖሊስ ሃይል የለንም በማለቱ ስብሰባው እንዳይካሄድ በማደናቀፍ ምክንያት መሆኑን
በተደራጀ ወንብድና የኣካል ጉዳት የደረሰባቸው የኣረና ኣባላት በከተማው ጤና ጣብያ ተመርምረው የራጀ ምርመራ እንደሚያስፈልጋቸውና ሆስፒታል እንዲወሰዱ በሃኪም የተሰጠ ትእዛዝ በፖሊስ ኣለመፈፀሙን፣
የተፈፀመው የወንብድና ተግባር ለማድበስበስ በሃሰት ክስ፣ በኣቶ ኣስገደ ገ/ስላሴና መም/ፍፁም ግሩም የተቀነባበረው ወንጀላ እየተፈፀመ መሆኑን ነው ።
ህ.ወ.ሓ.ትና መስተዳድሩ ወደዚህ የፖለቲካ ቅሌት የሚገፋፋቸው ያለው በዓረና የኣማራጭ ፖሊሲ ልዕልና መርበትበቱንና ወደ እራቆቱ የወጣ በጠራራ ፀሃይ የኣማራጭ ፓርቲ ወጣት መሪዎችን በማፈን ማንበርከክ መምረጡንና የትግራይ ህዝብና ወጣት ልጆቹ የከፈሉት መስዋእትነት ጭራሽ ከምድረ ትግራይ ጠራርጎ ለማጥፋት መቑረጡን የሚያሳይ እኩይ ተግባር በመሆኑ የዓረና ትግራይ ፓርቲ የተቃውሞ ድምፁን ከፍ በማድረግ ለትግራይ ህዝብና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ያሰማል፡፡ ዓረና ትግራይ የትግራይ ህዝብ የከፈለው የ17 ዓመታት የትግል ዘመን ብህ.ወ.ሓ.ት ተቀብሮ እንዳይቀር በማደስ የተነሳ ፓርቲ እንደመሆኑ በህ.ወ.ሓ.ት የሽብር ተግባር የማይታጠፍ መሆኑን በማረጋገጥ በህዝባችን ፊት የሚከፈለውን ሁሉ መስዋእትነት እየከፈልን ብፅናት የምንቀጥልበት መሆኑን ለመግለፅ ይወዳል፡፡
የዓዲግራት ከተማ ወጣቶች የተደረጁ ኣሸባሪ ወንጀለኞችን በመመከት የኣባለቶቻችን ህይወት ለመታደግ ያሳየው ድፍረት እንዲሁም የዕዳጋ ሓሙስ ከተማ ነዋሪዎችና የፋፂ ከተማ ነዋሪዎች ዓረና ለህዝቡ የቀረበው ጥሪ በማክበር ያሳያችሁት ኣክብሮትና ፍላጎት ኣክብሮታችን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ዓረና ትግራይ ፓርቲ በዚሁ የወንብድና ተግባር ሳይንበረከክ ከትግራይ ምስራቃዊ ዞን ህዝብ በኣጠቃላይና በዓዲግራትና ኣከባቢዋ የህዝብ ስብሰባ በመጥራት ከህዝቡ መምከር በፅናት እንደንቀጥልበት በእርግጠኝነት ለማረጋገጥ እንወዳለን፡፡
ጥር 18 ቀን 2006 ዓ/ም
መቐለ

ምንሊክ ሳልሳዊ:-ሃገሪቱን የሚያሰጋት የሃይማኖት አክራሪነት/አሸባሪነት ሳይሆን የፖለቲካ የበላይነት የፈጠረው አሸባሪነት ጽንፈኝነት እና አክራሪነት ነው::ጥላችሁን እንዳታምኑ እየተባለ ሃይማኖት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እንዲወጣ ለማድረግ መሞከር አክራሪነት ነው፡፡

«መጾም፣ መጸለይ፣ ሥርዓተ-አምልኮን መፈጸም ለሃይማኖቱ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንጂ አክራሪነት ሊባል አይችልም፤»…የአክራሪ ክርስትና ወይንም እስልምና ቡድን መኖር የክርስትና እና እስልምና ተከታዮችን በሙሉ «አክራሪ» አስብሎ ሊያስፈርጃቸው አይችልም::አክራሪ ተብሎ የሚፈረጀው የሚራመዱ የፖለቲካ ጡዘቶች በሰዎች ላይ ሌላ እምነትን በመጫን በግዳጅ እና በሃይል ሊያስገድዱ ሲሞክሩ ይህ ማለት አህበሽን እና ተሃድሶን በጥንታውያኑ እስልምና እና ተዋህዶ ላይ በኢትዮጵያ እንደተሞከረው ማለት ነው::

አክራሪነት አሉታዊ ትርጉም ሲኖረው የራስን እምነትና አመለካከት በሌሎች ላይለመጫን መሞከር ነው፡፡ ሃይማኖት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እንዲወጣ ለማድረግ መሞከር ራሱ አክራሪነት ነው፡፡ አክራሪነት የፖሊቲካ ገጽታ ያለው ነው፡፡ ኾኖም ግን ሃይማኖትን ማጥበቅ አክራሪነት አይደለም፡፡ሃይማኖት ፍጹም እውነታን በፍጹም እምነት ስለሚቀበል ከሌሎች ግላዊ አስተሳሰቦች የተለየ ነው፡፡ የሃይማኖት መገለጫዎችን መጠቀም የዚያን ሃይማኖት ጥልቀት የሚያሳይ እንጂ እንደ ችግርም የሚወሰድ ወይም አክራሪነት ሊኾን አይችልም፡፡ «መጾም፣ መጸለይ፣ ሥርዓተአምልኮን መፈጸም ለሃይማኖቱ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንጂ አክራሪነት ሊባልአይችልም፤» ይላሉ የዘርፉ ምሁራን፡፡

የአክራሪነትና የአጥባቂነት ፅንሰ ሐሶቦች በጥሩ ኹኔታ ተለይተው ተገልጸዋል፡፡ አንዳንድ ሰነዶች ወያኔም ለይስሙላ የገለበጣቸው ሰነዶቹ አክራሪነትንና አጥባቂነትን በአግባቡ ለይተውና ተንትነው ያስቀምጣሉ፡፡ በዚሁ መሠረትአጥባቂነትን፣ ‹‹የግል ሃይማኖትን ሃይማኖቱ በሚያዘው መሠረት ሳይንጠባጠብ ሁሉንም ትእዛዛት መፈጸም ነው፤» በማለት ሲፈታው አክራሪነትን ደግሞ፣ «ከራስ እምነት ወጥቶ ሌላውን መተንኮስና የሌሎችን ሃይማኖት መኖር አለማመንና አለመፍቀድወይም ሌሎቹን አስገድዶ የራስ እምነት ተከታዮች ለማድረግ መጣር ነው፤» ይላል፡፡ በተግባር ላይ አለመዋሉ እና በጣልቃ ገብነት መተርጎሙ ጉዳት አመጣ እንጂ::

ከዚህ ብያኔ ስንነሣ ክርስቲያንም ሆነ ሙስሊም ከርሱ ውጭ የኾኑትን የሌሎቹን መኖር የማይቀበልና ከግለሰቦቹ ፈቃድ ውጭ አስገዳጅ እስከኾነ ድረስ እርሱን አክራሪ ማለት ይቻላል፡፡መብትን መጠየቅ ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት መሸሽ አክራሪነት አይደለም:: በዚህ መልኩ አክራሪው ይህንኑ ድርጊት ሊፈጽም የተነሣውን ቡድን ብቻ እንጂ «አክራሪው ቡድን» የወጣበትን/የተገኘበትን ቤተ እምነት ሊወክል አይችልም፡፡ ስለዚህ በአለማቀፍ ደረጃ የአክራሪ ክርስትና እና እስልምና ቡድን መኖር የክርስትና እና እስልምና ተከታዮችን በሙሉ «አክራሪ» አስብሎ ሊያስፈርጃቸው አይችልም፤ ለሌላው ቤተ እምነትም እንዲሁ፡፡ ሃገሪቱን የሚያሰጋት የሃይማኖት አክራሪነት ሳይሆን የፖለቲካ የበላይነት የፈጠረው አሸባሪነት ጽንፈኝነት እና አክራሪነት ነው::ምንሊክ ሳልሳዊ

‹ከአቅሜ በላይ የሆነ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል መረጃ ደርሶኛል በፍጥነት ከተማውን መልቀቅ አለባችሁ››
የህወሃት/ኢህአዴግ የሃይል መንገድ የሚያሳየን ድርጅቱ የሐሳብ ምክነት እንዳለበት ነው

በአንድነት ፓርቲ የሶስት ወራት ህዝባዊ ንቅናቄ ላይ መሳተፍ መቻሌ አገሪቱን በመምራት ላይ ስለሚገኘው ጡንቸኛው ድርጅት ብዙ ነገሮችን በቅርበት ለማወቅ አስችሎኛል፡፡ወደ ደቡብ ክልል በማቅናት በወላይታ ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ የከፈልነው መስዋዕትነት መሪዎቻችን ምን ያህል የፓርቲዎችን ከህዝብ ጋር መገናኘት እንደሚፈሩ እንዳውቅ አድርጎኛል፡፡
ሹፌራችን ምንም በማያውቀው መንገድ ‹‹ፖለቲከኞቹን ወደዚህ ያመጣህው አንተ ነህ ››ተብሎ ተደብድቧል፣ጄኔሬተር የሸጠልን ነጋዴ ከሁለት መቶ ሜትር በላይ በሩጫ ተከትሎን እንደ ህጻን በሁለት ጉንጮቹ መንታ መንታ እያነባ የሸጠልንን ጄኔሬተር እንድንመልስለት ይህንን ባናደርግ ግን ንግዱ ተዘግቶ ልጆቹ እንደሚበተኑ ተማጽኖናል፡፡ታርጋ ባልለጠፈ ሞተር ሳይክል እላዬ ላይ ሊከመር ከነበረ ባለ ሞተር ያመለጥኩትም ሱቅ ውስጥ ዘልዮ በመግባቴ ነበር፡፡የከተማውን ፖሊስ ጣብያ የሚመሩ ሻለቃ ‹‹ከአቅሜ በላይ የሆነ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል መረጃ ደርሶኛል በፍጥነት ከተማውን መልቀቅ አለባችሁ›› በማለት በመኪናቸው በማጀብ ሸኝተውናል፡፡
እኛን በመተባበር ቅስቀሳ ላይ የተሰማሩ የአካባቢው ተወላጅ ዩኒቨርስቲ የሚማር ልጃቸው በምሽት ተጠልፎ ተወስዶባቸዋል፣በፍቼ ሁለት የአንድነት አባላት በአስራ ስድስት ሰዎች ተቀጥቅጠዋል፡፡አስገራሚው ነገር ይህንን ቅጥቀጣ የመሩት የአካባቢው የፍትህ ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑ ሰው ናቸው፡፡በሌሎቹም ቦታዎች እስራት፣ድብደባ፣ማስፈራሪያና ንብረት ቅሚያ በሽበሽ ነበር፡፡
ሰሞኑን በአረና አባላትና አመራሮች ላይ የደረሰው በደል ከላይ ለማስቀመጥ የሞከርኩትን ክስተት መለስ ብዬ እንዳስታውሰው አድርጎኛል፡፡የህወሃት ሰዎች የድርጅቱ መስራች የነበሩትን የእድሜ ባለጸጋ ከትግራይ ህዝብ ባህል ባፈነገጠ መልኩ አቶ አስገደን ደብድበዋል፣ ህወሃትም በዚህ ድርጊቱ ታሪኩን አራክሷል፡፡በማህበራዊ ድረ ገጾች የምናውቀው አብርሃ ደስታም ከድንጋይ አላመለጠም፡፡
እነዚህ ነገሮች ምን ይነግሩናል? በእኔ መመዘኛ ሰላማዊ ትግል አያዋጣም ለሚሉ ሰዎች ይህ ድርጊት ጥዑም ዜማ ሊሆናቸው አይችልም፡፡ይህ ድርጊት በግልጽ የሚነግረን ህወሃት/ኢህዴግ ሰላማዊ ትግልን ከመሳሪያ በላይ እንደሚፈራው፣የሰላማዊ ትግል ቋንቋ እንደ ባቢሎን ሰዎች ድብልቅልቅ እንደሆነበት ነው፡፡
ህወሃትን የትግራይ በማድረግ ህዝቡን በአንድ ጠርሙስ የከተትን ሰዎችም አረና ላይ የደረሰው ነገር ህወሃት በህዝቡ የተፈጠረ የህዝቡ ወኪልና ንብረትነቱም ለህዝቡ ሳይሆን ለራሱ ብቻ መቆሙን እንድንመለከት ያደረገ በመሆኑ በህወሃትና በትግራይ ህዝብ መካከል የሰማይና የምድር ያህል ርቀት መኖሩን መገንዘብ ይገባናል፡፡
ህወሃት/ኢህአዴግ በተቃዋሚዎቹ ላይ የሚሰነዝረው የሰለጠነ አስተሳሰብ የሌለው መሆኑን በመረዳትም ትግሉ የበለጠ የሚጠናከርበትን መንገድ ተቃዋሚዎች ተቀራርበው መዘየድ ይኖርባቸዋል፡፡ምን አልባት አረና ላይ የተወረወረው ደንጊያ ነገ ወደ መሳሪያ ሊለወጥ ይችላል፡፡ያ ካምፕ ያለው ይህ በመሆኑም ተቃዋሚዎች ለሚመጣው ሁሉ ዝግጁ መሆን ግድ ይላቸዋል፡፡
ለህወሃት/ኢህአዴግ ማዘን ይገባናል፣የድርጅቱ አባላትና አመራሮች ደግሞ ማፈር ይጠበቅባቸዋል፡፡ላለፉት 23 አመታት አገሪቱን የመራ ፓርቲ እንዴት እስካሁን በደደቢት ቋንቋ ይናገራል? ለድርጅቱ የምናዝነው ከመለስ ፊትና ኋላም ቢሆን ከምክነት ባለመዳኑ ጭምር ነው፡፡
Dawit Solomon

Image

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከተማችን ቁጥራቸው እየበረከተ የመጡት ቀያይ ሲኖትራክ ከባድ መኪናዎች በመንገደኞች ላይ አሰቃቂ አደጋ እያደረሱ ሲሆን ነዋሪዎችም “ቀይ ሽብር” የሚል ቅጽል ስም እንደሰጧቸው ይናገራሉ፡፡

ኮልፌ አካባቢ በ350 ብር ቤት ተከራይታ የምትኖረው የ31 ዓመቷ ማህሌት አሸናፊ፤ በወሲብ ንግድ ነበር የምትተዳደረው፡፡ ቀን ቀን የሁለት ዓመት ልጇን ስትንከባከብ ትውልና ምሽት ላይ ልጇን ለሞግዚት ሰጥታ “ቢዝነስ” ትወጣለች። ማህሌት ቦሌ ሩዋንዳ ከሚኖሩት ወላጆቿ ጋር የተለያየችው በእርግዝናዋ ሳቢያ ነው፡፡ ዘወትር “ቤተሰቤን ያጣሁበት ነው” ለምትለው ልጇ ያላት ፍቅር ልዩ ነው፡፡ ማታ ማታ ለ”ቢዝነስ” ስትወጣ እንኳን እንደሌሎች ባልደረቦቿ አታድርም፡፡ ቢዝነስ ቀናትም አልቀናትም ቢበዛ እስከ ሰባት ሰዓት አምሽታ ልጇ ጋ ትመለሳለች፡፡
ዘንድሮ አዲስ ዓመት ላይ ከወሲብ ንግድ ወጥታ ሌላ ስራ ለመቀጠር የወሰነችውም ለልጇ በማሰብ ነው – “እያደገ ሲመጣ ስሜቱ ይጎዳል” በሚል፡፡ እናም በአጭር ጊዜ ውስጥ ሰፈሯ በሚገኝ ካፌ ውስጥ ተቀጥራ መስራት ጀመረች፡፡ ለረዥም ጊዜ አይታቸው ከማታውቀው እናቷ መልዕክት የደረሳትም ይሄኔ ነው፡፡ በጠና መታመማቸውንና ዓይኗን ለማየት እንደጓጉ ሰማች፡፡ የእናትን አንጀት ታውቀዋለችና አላስቻላትም፡፡ ወደ እናቷ ቤት ለመሄድ ተነሳች፡፡ ግን ፍርሃት ፍርሃት ብሏት ነበር፡፡ “ልቤ ፈራ—እናቴ ሞታ እንዳይሆን…” ስትል ስጋቷን ለልጇ ሞግዚት አካፍላታለች፡፡ ከቤት ከመውጣቷ በፊት ልጇን አገላብጣ ሳመችው – ሩቅ አገር እንደሚሄድ ሰው፡፡ ምናልባት እናቷ አርፈው ከሆነ ማደርም ሊኖር ይችላል ብላ ያሰበችው ማህሌት ካፌ ለምትሰራ ጓደኛዋ ልጇን እንድታይለት አደራ ስትላት ለምን ይዘሽው አትሄጅም የሚል ሃሳብ አቅርባላት ነበር፡፡ ማህሌት ግን “ምናልባት ችግር ካለ በእኔ ብቻ ይለፍ” አለችና ወደ እናቷ ቤት ለመሄድ ጉዞ ጀመረች፡፡
በተለምዶ 18 ማዞሪያ በሚባለው አካባቢ መንገድ ለመሻገር ቆማ ሳለ፣ ከጦር ሃይሎች አቅጣጫ የመጣ አንድ ሲኖትራክ መንገድ ይስትና ማህሌትንና ሌሎች ሦስት መንገደኞችን ይገጫል፡፡ እሷ ወዲያው ህይወቷ ያለፈ ሲሆን የቀሩት ከባድና ቀላል ጉዳት እንደደረሰባቸው የፖሊስ መረጃ ያመለክታል፡፡
የ26 ዓመቱ ወጣት ቴዎድሮስ አበራ፤ የ4ኛ አመት ኢንጂነሪንግ ተማሪ ነበር፡፡ ለቤተሰቡ ብቸኛ ልጅ ስለሆነ ወላጆቹ እንደ አይናቸው ብሌን ነው የሚያዩት፡፡ ባለፈው ህዳር አንድ ጠዋት ላይ ነው፡፡ ከዩኒቨርስቲ ጓደኞቹ ጋር የጥናት ቀጠሮ ቢኖረውም መጀመርያ የታመሙትን እናቱን ወይዘሮ እቴነሽ ሳህሉን ወደ ሆስፒታል መውሰድ ነበረበት፡፡ ሳሪስ አዲሱ ሰፈር ከሚገኘው መኖርያ ቤታቸው እናቱን በሃች ባክ መኪና ይዞ ወጣ፡፡ ስለመንገዱ መጨናነቅ ለእናቱ እያወራ ነበር የሚያሽከረክረው፡፡ ዘንባባ ሆስፒታል መታጠፊያ ጋር ሲደርሱ ከፊት ለፊት የሚመጣው ሲኖትራክ ያላማራቸው እናት፤ ልጃቸው ጥግ እንዲይዝ ይነግሩታል፡፡ ጥግ ከመያዙ በፊት ግን ያለአቅጣጫው እየተክለፈለፈ የመጣው ከባድ መኪና፣ ሃች ባክዋን በሹፌሩ በኩል ክፉኛ ገጭቶ ከመንገዱ ውጭ ወረወራት፡፡
የቴዎድሮስ እናት ወ/ሮ እቴነሽ ሳህሉ፤ ሆስፒታል ከገቡ ከረዥም ሰዓት በኋላ ነበር ራሳቸውን ያወቁት። ሲነቁ አንድ እግራቸው ከጥቅም ውጭ ሆኗል። ወዲያው ስለልጃቸው መጠየቅ ጀመሩ፡፡ ማንም እውነቱን ለመንገር አልደፈረም – በድንጋጤ አንድ ነገር እንዳይሆኑ በመፍራት፡፡
አደጋው በደረሰ በአስረኛው ቀን እናት ልጃቸው መሞቱን ተረዱ፡፡ በድንጋጤ ዳግም ራሳቸውን ስተው ለተጨማሪ አስር ቀን እዚያው ሆስፒታል ውስጥ ተኙ፡፡ አሁንም ስለአደጋው ሲያስታውሱ ስቅስቅ ብለው የሚያለቅሱት ወ/ሮ እቴነሽ፤ “ምናለ እኔን ወስዶ ልጄን ቢያተርፍልኝ” እያሉ በቁጭት ይቆዝማሉ፡፡
ህዳር 18 ቀን 2006 ዓ.ም ከሌሊቱ 11፡00 ሰዓት ገደማ ነው፡፡ ሃይሉ አበራና ቴዎድሮስ አበራ የተባሉ ወጣት የጐዳና ተዳዳሪዎች፣ የዘወትር ማረፍያቸው በሆነውና ፒያሳ በሚገኘው ጊዮርጊስ ቤተክርስትያን ደጃፍ ላይ ጐናቸውን አሳርፈዋል፡፡ አቶ አበራ ተሰማ እና አቶ ሞላ አበራ ደግሞ ቤታቸው እዚያው አካባቢ ሲሆን ወደ ስራ ሲሄዱ “ሰላም አውለኝ” ለማለት ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን ጎራ ይላሉ፡፡
ውጭ ደጃፉ ላይ እንደቆሙም አንድ ሲኖትራክ ከየት መጣ ሳይባል መንገድ ስቶ አራቱንም ይገጫቸዋል፡፡ ከፖሊስ በተገኘው መረጃ መሰረት፤ ሁለቱ የጎዳና ተዳዳሪዎችና አቶ አበራ ተሰማ ወዲያው ህይወታቸው ሲያልፍ፣አቶ ሞላ አበራ የተባሉት ግለሰብ የአካል ጉዳት ደርሶባቸው በህይወት ተርፈዋል፡፡
የካቲት 1 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ አምስት ሰዓት ገደማ፣ በቦሌ ክ/ከተማ ልዩ ቦታው በሻሌ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት አካባቢ አንዲት ባጃጅ፣ ሹፌሩን ጨምሮ ስድስት ሰዎችን ጭና እየተጓዘች ነበር – ዚያዳ አስፋው፣ ብሩክ ሲሳይ፣ ገብርኤላ ሙሉጌታ፣ ክርስቲያን ክፍሉ፤ መንግስቱ ጫፎ እና የባጃጁ ሹፌር። ባጃጇ ከሰሚት ተነስታ ፊጋ ተብሎ ወደጠራው ሰፈር እየተጓዘች ነበር፡፡ የባጃጁ ሹፌር “”ዛሬ ቀኑ ይከብዳል አይደል?” በማለት ባነሳው ወግ መነሻነት ጨዋታው ደርቶ ነበር፡፡ ድንገት ከተቃራኒ አቅጣጫ የመጣው ሲኖትራክ ግን እነሱንም ጨዋታቸውንም በታተናቸው፡፡ በአደጋው ሶስት ሰዎች ህይወታቸው ሲያልፍ፣ በሶስቱ ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው ፖሊስ ገልጿል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከተማችን ቁጥራቸው እየበረከተ የመጡት ቀያይ ሲኖትራክ ከባድ መኪናዎች በመንገደኞች ላይ አሰቃቂ አደጋ እያደረሱ ሲሆን ነዋሪዎችም “ቀይ ሽብር” የሚል ቅጽል ስም እንደሰጧቸው ይናገራሉ፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የትራፊክ አደጋ ምርመራ ቡድን መሪ፣ ረዳት ሳጅን ቶሎሳ፤ ሲኖትራኮች ካለፈው ነሐሴ ወር ጀምሮ በየወሩ ከስድስት እስከ ስምንት አደጋዎች እያደረሱ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ ረዳት ሳጅኑ ለአደጋው መብዛት እንደምክንያት ከጠቀሷቸው መካከል፤ የሹፌሮች ብቃት ማነስ፣ የተሽከርካሪዎቹ ፍሬን ቶሎ መሞቅ፣ ከተፈቀደላቸው ክብደት በላይ መጫንና በሃሰተኛ መንጃ ፍቃድ ማሽከርከር ይገኙባቸዋል። ሲኖትራኮች የተፈቀደላቸው የጭነት መጠን 132 ኩንታል እንደሆነ የሚናገሩት ረዳት ሳጅኑ፤ አብዛኛዎቹ ግን ከሁለት መቶ በላይ ኩንታል እየጫኑ መንቀሳቀሳቸው ለአደጋው መባባስ አስተዋፅኦ አድርጓል ብለዋል – ረዳት ሳጅን ቶሎሳ። አንዳንድ የሲኖትራክ አሽከርካሪዎች በበኩላቸው፤ የመኪኖቹ ጥራት ላይ ጥርጣሬ እንዳላቸው ይናገራሉ። ሲኖትራክ የቻይና ስሪት እንደሆኑ የጠቀሱት ረዳት ሳጅን ቶሎሳ፤ የመኪኖቹን የጥራት ደረጃና አጠቃላይ ይዞታ በተመለከተ ከአስመጪዎቹ ጋር በቅርቡ ውይይት እንደሚካሄድ ተናግረዋል። ሲኖትራክ የተባሉት ከባድ መኪኖች በአብዛኛው ቻይናዎች በተሰማሩባቸው የመንገድና የባቡር ሃዲድ ፕሮጀክቶች ላይ እያገለገሉ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡
addis admass

ሪፖርተር፡- ዶ/ር ነጋሶ ፖለቲካ በቃኝ በማለት አንድነትን የለቀቁት የአቶ ሌንጮ ልዩ አማካሪ ሆነው ለመሥራት ተስማምተው ነው ይባላል፡፡
ዶ/ር ነጋሶ፡- ሌንጮን ያገኘሁት ከሦስት ዓመት በፊት አንድነት ፓርቲ ስዊድን ጋብዞኝ ሄጄ ነበር፡፡ ከዚያ ስመለስ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ማኅበር ጋብዞኝ ኖርዌይ ሄድኩኝ፡፡ ሌንጮ የሚኖረው እዚያ ነበር፡፡ የሥጋ ዘመዴ በመሆኑ ደውዬ አግኝቼዋለሁ፡፡ ግን ከዘመድ አዝማድ ጥያቄ ውጪ ምንም ዓይነት የፖለቲካ ውይይት አላደረግንም፡፡ ከዚያ በፊት ግን እኔ ፓርላማ እያለሁ በኢሜይል እንገናኝ ነበር፡፡ መለስ ከልክሎት ነው መሰለኝ አቋርጦ ጠፋ፡፡ ምንም ዓይነት ግንኙነት የለንም፡፡ እንዲያውም ሰሞኑን አንድ ሚዲያና ዶ/ር መረራ ደውለው ‹‹ሌንጮ መጥቷል ይባላል እውነት ነው?›› ብለው ጠየቁኝ፡፡ እንዳልሰማሁና ከነሱ መስማቴን ከመግለጽ ውጪ ምንም ዓይነት ግንኙነት የለኝም፡፡

Image

በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ወለጋ ዞን ደንቢዶሎ ከተማ ውስጥ ጳጉሜ 3 ቀን 1935 ዓ.ም. ከቄስ ጊዳዳ እና ከወ/ሮ ኢንሲ ሾሊ የተወለዱት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ በ73 ዓመታቸው ለ45 ዓመታት ከቆዩበት የፓርቲ ፖለቲካ እንቅስቃሴ ራሳቸውን ማግለላቸውን ሰሞኑን ይፋ አድርገዋል፡፡

ለወላጆቻቸው አራተኛ ልጅ የሆኑት ዶ/ር ነጋሶ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በተወለዱበት አካባቢ ከተከታተሉ በኋላ፣ ወደ አዳማ በመምታት ከዘጠነኛ እስከ 11ኛ ክፍል በባይብል አካዳሚ ተምረዋል፡፡ በወቅቱ በመላ አገሪቱ የነበሩ የ11ኛ ከፍል ተማሪዎች በውጤታቸው ሲመረጡ እሳቸውም በመመረጣቸው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ውስጥ በነበረው በዕደ ማርያም ትምህርት ቤት ገብተው 11ኛ እና 12ኛ ክፍል ተምረዋል፡፡ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሔራዊ ፈተና ሳይፈተኑ በቀጥታ ወደ ኤዱኬሽን ፋኩልቲ በመግባት የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በታሪክ የትምህርት ዘርፍ አግኝተዋል፡፡ ወደ ጀርመን በመጓዝም ሁለተኛ ዲግሪያቸውንና የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ወስደዋል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ላለፉት 45 ዓመታት በነበራቸው የፖለቲካ ተሳትፎና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ ታምሩ ጽጌ አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- በፖለቲካ ውስጥ መሳተፍ የጀመሩት መቼና እንዴት ነበር?

ዶ/ር ነጋሶ፡- አሥረኛ ክፍል እያለሁ በክረምት ወደ ደንቢዶሎ ስሄድ አንድ ሁኔታ ተፈጠረ፡፡ በአካባቢው ከተለያዩ ትምህርት ቤቶችና ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎች ለዕረፍት ይመጣሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ተሰባሰብንና ይኼንን የክረምት ወራት ለምን ተቀምጠን እናሳልፋለን? ለምን አናስተምርም? በማለት ድራማ አዘጋጀን፡፡ ድራማው የአርሶ አደሩን ችግር የሚገልጽ ነበር፡፡ ነገር ግን ድራማውን እንዳናሳይ የአውራጃው ሹም ከለከለን፡፡ በወቅቱ የፓርላማ አባላት ምርጫ የሚደረግበት ጊዜ ተቃርቦ ስለነበር ድራማው የተከለከለው ችግር ይፈጥራል በሚል ተሰግቶ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን ምርጫው ደረሰና ግለሰቦች ለፓርላማ አባልነት መወዳደር ጀመሩ፡፡ ፊታውራሪ ገነነ በዳኔ፣ ከአንፊሎ ደግሞ አቶ ከበደና ሲሜንሶ ዴንጋ የሚባሉ ዕጩ ተወዳዳሪዎች ለውድድሩ ቀረቡ፡፡ በወቅቱ የምርጫ ድምፅ ይሰጥ የነበረው በአንድ ሳጥን ውስጥ ሳይሆን በተወዳዳሪዎቹ ልክ ይዘጋጅና ምሥላቸው ይለጠፍበታል፡፡ እንዳሁኑ ድምፅ የሚሰጠው በአንድ ቀን አልነበረም፡፡ ሳምንቱን ሙሉ ነበር፡፡ አርሶ አደሩ ተመችቶት መጥቶ እስከሚመርጥ የምርጫ ጊዜው ለአንድ ሳምንት የሚቆይ ቢሆንም፣ ከተወዳዳሪዎቹ አንዱ የሆኑት ሲሜሶ ዴንጋ ውድድሩን በአንድ ቀን ድምፅ አሰጣጥ አሸነፉ፡፡ የማሸነፋቸው ሚስጥር ደግሞ የቅስቀሳ ዘዴያቸው ነበር፡፡ አቶ ሲሜሶ ሦስት ፍሬ ባቄላ ማለት በጣም ያረረ፣ መካከለኛና ጥሬ ይዘው ወደ አርሶ አደሩ በመሄድ ቅስቀሳ ይጀምራሉ፡፡ አርሶ አደሮቹን በመሰብሰብ ‹‹ይኼንን ባቄላ ተመልከቱ፣ የእናንተ ኑሮ የትኛውን ይመስላል?›› በማለት ሲጠይቋቸው ‹‹የኛ ኑሮማ ያረረውን ባቄላ ነው የሚመስለው፤›› ሲሏቸው፣ ‹‹እኔን ከመረጣችሁኝ የፓርላማ አባል ስለምሆን፣ ለንጉሡ በማስረዳት ይኼንን ኑሯችሁን እቀየርላችኋለሁ፤›› በማለት ያስረዳሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ለአንድ ሳምንት እንዲመርጡ ይደረጉ የነበሩት አርሶ አደሮች በአንድ ቀን የአቶ ሲሜሶን የድምፅ መስጫ ኮሮጆ ሞሉት፡፡ በዚህም ምክንያት ‹‹ይኼ ሰውዬ መንግሥትንና ሕዝብን እያጣላ ነው›› በማለት አቶ ሲሜሶን የአውራጃው ሹም ያስሯቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ እዚያ የነበርን ተማሪዎች፣ መምህራንና የአገር ሽማግሌዎች ሰላማዊ ሠልፍ አደረግን፡፡ ወደ አውራጃ ገዥው ቢሮም ሄደን ትክክል አለመሆናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ ሰጠናቸው፡፡ በዚህ ጊዜ አስተዳዳሪው ‹‹እናንተ ብዙ ናችሁ፡፡ ልጆችም ናችሁ፡፡ እኔ ከልጆች ጋርም አልነጋገርም፡፡ የበሰሉና ያገር ሽማግሌዎች ነገ ይምጡ፤›› ሲሉን ተመለስን፡፡ በሚቀጥለው ቀንም የተላኩት ሽማግሌዎች ታሰሩ፡፡ ከሁለት ወራት ቆይታ በኋላ ፓርላማ ሲከፈት ጥቅምት 23 ቀን ተለቀቁ፡፡ ይኼ ወደ ፖለቲካው የመግቢያዬ አንዱ መንገድ ነበር፡፡

ሪፖርተር፡- ከዚያስ?

ዶ/ር ነጋሶ፡- በወቅቱ የተማሪዎች እንቅስቃሴና ሠልፍ ነበር፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ማኅበር ጉባዔ ምርጫ ነበር፡፡ በዚህ ውስጥ እኔም እሳተፍ ነበር፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ማኅበር ከማናቸውም አድሎአዊ አሠራር የፀዳ ነበር፡፡ አንድ ዓይነት ዓላማና አቋም ነበረን፡፡ ‹‹የሕዝቦች መብት ይከበር፣ የሠራተኞች መብት ይከበር፣ የአርሶ አደሩ መብት ይከበር፣ ንጉሣዊ አገዛዝ አንፈልግም፣ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ይመሥረት፣ የሴቶችና የሃይማኖቶች እኩልነት ይከበር፤›› የሚሉትን ዓላማዎች ይዘን ነበር የምንቀሳቀሰው፡፡ ሆኖም ግን እኔ በዕደ ማርያም ትምህርት ቤት ስገባ ሌላ ሁኔታ እየተፈጠረ ነበር፡፡ የሜጫና ቱለማ (የኦሮሞ ማኅበር) ተመሥርቶ ነበር፡፡ የብሔራዊ ፊደል ሠራዊት ሊቀመንበር የነበሩት ጄኔራል ታደሰ ብሩ ሊቀመንበሩ ነበሩ፡፡ የማኅበሩ ዓላማ በልማት ላይ የተመሠረተ ነበር፡፡ ማኅበሩ ባጭር ጊዜ ዝና አገኘ፡፡ ከተለያዩ የኦሮሚያ አካባዎች ተመርጠው የፓርላማ አባል የነበሩ ሁሉ የማኅበሩ አባል ሆኑ፡፡ እኔም የማኅበሩ አባል ሆንኩኝ፡፡ በወቅቱ 12ኛ ክፍል ነበርኩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድ የማኅበሩን ሊቀመንበር ጄኔራል ታደሰ ብሩን ጠርተው የማኅበሩን እንቅስቃሴ እንዲያቆሙ ነገሯቸው፡፡ ‹‹ይኼ ሕዝብ ባህር ነው፡፡ ከተማረ ስለሚያጥለቀልቀን የፊደል ሠራዊት ሌላ ሌላ የምትለውን አቁም፤›› አሏቸው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጄኔራል ታደሰ ኦሮሞ መሆናቸውን አላወቁም፡፡ በዚህ ጊዜ ጄኔራሉ፣ ‹‹እኛ ለልማት እየተንቀሳቀስን እንዴት አቁሙ እንባላለን›› በማለት ነገሩን ወደ ፖለቲካ በመለወጥ መቀስቀስ ጀመሩ፡፡ በዚህ ጊዜ ፖለቲካው መስመር መያዝ ጀመረ፡፡ የመጀመሪያ ዓመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለሁ ‹‹ኩዴታ ታቀደ›› የሚባል ነገር ተሰማ፡፡ የመፈንቅለ መንግሥቱ ዋና ዓላማ አፄ ኃይለ ሥላሴን ለመግደል ነበር፡፡ በ‹‹ኩዴታው›› ውስጥ የተሳተፉት ጄኔራል ታደሰ ብሩና ጓደኛቸው መሆናቸው ሲነገር ጄነራሉ ሸፈቱ፡፡ በዚህ ጊዜ ጳጳሱ አቡነ ቴዎፍሎስ አማልደው ከንጉሡ ጋር አስታረቁዋቸው፡፡ ንጉሡ ከታረቁ በኋላ ጄኔራሉ የትም እንዳይንቀሳቀሱ የቁም እስር ፈረዱባቸው፡፡ ሜጫና ቱለማ ማኅበርም ተከለከለ፡፡ በዚህ ጊዜ ተማሪዎች ተሰባሰብንና ሌላ ማኅበር አቋቋምን፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ሆነን ‹‹ዴዴሳ የዕድገት ማኅበር›› የሚል አቋቋምን፡፡ ዓላማው ከየጠቅላይ ግዛቱ ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ለሚገቡ አዳሪ ተማሪዎች ሆስቴል ማሠራት ነበር፡፡ ትንሽ እንደተንቀሳቀስን እሱም ተከለከለ፡፡ ከዚያ በኋላ በዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ የተማሪዎች ማኅበር ውስጥ እየተሳተፍን፣ ጥቂት ተማሪዎች ተሰባሰብንና ‹‹ሜጫና ቱለማ ታገደ፣ ዴዴሳ የዕድገት ማኅበርም ታገደ፣ ለምን በማለት ተመካከርን፡፡ በወቅቱ ባሌ ጎባ አካባቢ የኦሮሞ ነፃ አውጪ የሚባል ተቋቁሟል የሚባል ነገር ስለነበር እሱም ተፅዕኖ አሳድሮብን ነበር፡፡ እኛ ለምን ለኦሮሞ ሕዝብ ነፃነት አንታገልም? የሚል ውይይት አደረግን፡፡ ሴቶችም፣ ሃይማኖቶችም፣ አርሶ አደሮችም ለእኩልነታቸው መታገል አለባቸው የሚል አቋም ያዝን፡፡ እነ ጥላሁን ግዛውና ዋለልኝ መኮንን የብሔር ጥያቄ ያነሱበት ወቅትም ነበር፡፡ ያ ያ ተፅዕኖ አሳድሮብን ስለነበር የኦሮሞ ሕዝብ መታገል አለበት በማለት መንቀሳቀስ ጀመርን፡፡ ዲማ ነገዎ (ዮሐንስ ነገዎ) የኦነግ የመጀመሪያው ሊቀመንበር ነበር፡፡ አዲሱ ቶሎሳ፣ ፀጋዬ ነመራ፣ ቦሩ አልዴቻ፣ በቀለ ወልዴ ሆነን መንቀሳቀስ ጀመርን፡፡ ‹‹ቮይስ ኦፍ ኦሮሞ አጌንስት ታይራኒ›› (ፀረ አምባገነንነት የኦሮሞዎች ድምፅ) በሚል በታሪክ ጉዳይ፣ በመሬት ይዞታ ጉዳይ፣ በግብር ጉዳይ፣ በመንግሥት ውስጥ የኦሮሞ ተሳትፎ መድልአ፣ የቋንቋና ሌሎችን ያካተተ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ ተበተነ፡፡ እኔ የታሪኩን ጉዳይ ጽፌያለሁ፡፡ በዚህ ጊዜ እነ ባሮ ቱምሳ (የቄስ ጉዲና ወንድምና የኦነግ መሥራች ከነበሩት አንዱ) ናቸው የበተኑት ተብለው ታሰሩ፡፡ ወረቀቱ በብዛት በከፍተኛ ትምህርት ቤቶች ተበትኖ ስለነበር፣ በእነ መረራ ጉዲና ላይም ተፅዕኖ አሳድሮ በአምቦ አካባቢና በተለያዩ አካባቢዎች ባሉ ትምህርት ቤቶች እንቅስቃሴ ተጀመረ፡፡ በክረምት 1966 ዓ.ም. ኦነግ ሊመሠረት የቻለውም በዚያ እንቅስቃሴ አማካይነት ነው፡፡

ሪፖርተር፡- እርስዎ የኦነግ አባል የሆኑት በዚያ ጊዜ ነው?

ዶ/ር ነጋሶ፡- እኔ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ በነበርኩ ጊዜ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መማክርት ጉባዔ አባል ነበርኩ፡፡ በሁሉም እንቅስቃሴ እሳተፍ ነበር፡፡ በመካነ ኢየሱስ በኩል ጀርመን አገር የትምህርት ዕድል ተገኝቶልኝ ስለነበር ወደ ጀርመን ሄድኩኝ፡፡ ይኼ የሆነው የዩኒቨርሲቲ ትምህርቴን ጨርሼ በመምህርነትና በዳይሬክተርነት ወደ ወለጋ ተመልሼ አይራ ትምህርት ቤት ከሠራሁ በኋላ ማለት ነው፡፡ በ1966 ዓ.ም. አብዮቱ በተጀመረበት ወቅት ጀርመን ነበርኩኝ፡፡ አንድ ነገር ለማስታወስ የምፈልገው የትምህርት ዕድሉን አግኝቼ ወደ ጀርመን ለመሄድ ፓስፖርት ለማውጣት አዲስ አበባ ስመጣ (በክረምት 1966)፣ እነ ሌንጮ ለታ፣ ዲማ ነገዎ፣ አዲሱ ቶሎሳ ቀን ቀን አብረውኝ ይውሉና ማታ ማታ ይጠፉብኛል፡፡ ‹‹የት ነው የምትጠፉት?›› ብዬ ጠየቅኳቸው፡፡ ኦነግን በማቋቋም ላይ መሆናቸውንና እነ ታደሰ ብሩም የቁም እስረኛ ከሆኑበት ሐረር መፈታታቸውን ነገሩኝ፡፡ ይኼንን ከመስማቴ ውጪ አባል አልሆንኩም፡፡

ሪፖርተር፡- ጀርመን ከሄዱ በኋላ ግን የፖለቲካ ተሳትፎ ነበረዎት፡፡

ዶ/ር ነጋሶ፡- የሄድኩት ሁለተኛ ዲግሪዬን ጨርሼ ለመመለስ ነበር፡፡ በወቅቱ ግን ቀይ ሽብር በመጀመሩ መመለስ አልቻልኩም፡፡ ጀርመን ውስጥ ከሐረር፣ ከባሌና ከተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች ለትምህርት የሄዱ ተማሪዎች (የጄኔራል ዋቆ ጉቱ የባሌ እንቅስቃሴ ቶኩቹማ መሪ የነበሩ) ነበሩ፡፡ በ1966 ዓ.ም. ብዙ እንቅስቃሴዎች ነበሩ፡፡ እዚህ እነ ኦነግ ይቋቋማሉ፡፡ መኢሶንና ኢሕአፓ አገር ቤት ለመግባት ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ጀርመን አገር ደግሞ የኦነግ፣ የመኢሶንና የኢሕአፓ ደጋፊዎች አሉ፡፡ ማኅበርም መሥርተዋል፡፡ የኢሕአፓ ተማሪዎች ማኅበር ጄኔራል ዋቆ ጉቱን ጋብዞ (በክረምት 1966 ማለት ነው) ነበር፡፡ በወቅቱ ጄኔራል ዋቆን አጅበው የሄዱና እዚያው ጀርመን የቀሩ እኔ እንደሄድኩኝ አገኙኝ፡፡ ስለአገር ቤት ሁኔታ ጠየቁኝና ነገርኳቸው፡፡ እኔ የሄድኩት በ1967 ዓ.ም. መስከረም ወር ነው፡፡ ከሄድኩኝ ከሦስት ወራት በኋላ ተሰባስበን አንድ መጽሔት በቁቤ ማዘጋጀት እንዳለብን ወሰንን፡፡ መጽሔቱን አዘጋጀንና በብዙ የአውሮፓ አገሮች ጭምር መዳረስ ጀመረ፡፡ በዚህ መጽሔት አማካይነት ሰው መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ ቀጥሎ ‹‹ለምን ማኅበር አናቋቁምም?›› ተብሎ በጀርመን ‹‹የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር›› የሚል አቋቋምን፡፡ እኔ አመራር ነበርኩ፡፡ በክረምት 1967 ዓ.ም. ደግሞ ‹‹የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር በአውሮፓ›› የሚል ሌላ ማኅበር አቋቋምን፡፡ በዚያም ውስጥ እ.ኤ.አ. እስከ 1980 ድረስ ነበርኩኝ፡፡ እ.ኤ.አ. በ1977 ዲማ ከሴኔጋል ወደ ጀርመን መጥቶ ነበር፡፡ የኦነግ መሥራች ስለነበር ጀርመን የመጣበት ዓላማ የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበርንና የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር በአውሮፓ አባላትን አሳምኖ የኦነግ አባል ለማድረግ ነበር፡፡ ስለኦነግም ገለጻ አደረገ፡፡ እኔም በማኅበሩ በኩል አባል ሳልሆን ለኦሮሞ ነፃነት ስል እረዳ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. በ1980 ወደ አገር ቤት ለመመለስ ስለማልችል የኦነግ አባል ለመሆንና እነሱ ወዳሉበት አካባቢ ሶማሊያ፣ ጂቡቲ፣ ኬንያ ወይም ሱዳን ሄጀ ለመታገል ጥያቄ አቀረብኩኝ፡፡ እነሱ ግን፣ ‹‹አባል ነህ እዚያው ቆይተህ ትረዳለህ›› በማለት የኦነግ ወኪል አደረጉኝ፡፡ አንድ ዓመት ሳልቆይም በተማሪዎች ማኅበር ውስጥ ጭቅጭቅ ተፈጠረ፡፡ የእኔ ሐሳብ ሁሉም ተማሪዎች ኦነግን እንዲደግፉ ለማድረግ ነበር፡፡ መኢሶን ያቋቋመው የኦሮሞዎች ማኅበር ነበር፡፡ እኔ የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር በአውሮፓ ከእነሱ ጋር መዋሀድ አለበት የሚል አቋም ያዝኩኝ፡፡ የኦነግ ደጋፊ ማኅበር አባላት ‹‹እንዴት ከእነሱ ጋር እንዋሀድ ትላለህ? ጎበና ከሀዲ ሆንክ እነሱ ጎበናዎች ናቸው አሉ፡፡ የመኢሶን ልጆች ከደርግ ጋር ይሠሩ ስለነበር ጎበናዎች (ከሀዲዎች) ናቸው ይባሉ ነበር፡፡ ‹‹እንዴት ከእነሱ ጋር ትሠራለህ?›› በማለታቸው ማኅበሩን ትቼ ወጣሁ እ.ኤ.አ. በ1981 ከኦነግ አባልነቴ ራሴን አሰናበትኩ፡፡

ሪፖርተር፡- ከዚያ ወዴት ሄዱ?

ዶ/ር ነጋሶ፡- እ.ኤ.አ. እስከ 1984 ድረስ ምንም ዓይነት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ሳልገባ ቆየሁ፡፡ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች ወደ ጀርመን አገር ከሄዱ ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን የዕርዳታ ድርጅት አቋቋምን፡፡ እ.ኤ.አ. በ1985 የኦነግ ደጋፊ የነበረው አንደኛው የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር ለሁለት ተከፈለና አንደኛው ጎበና ነው ሲለው ከነበረው መኢሶን ካቋቋመው የኦሮሞ ተማሪዎች ማኅበር ጋር ተቀላቀለ፡፡ በዚህ ጊዜ እኔ እንድመለስ ጠየቁኝ፡፡ ተመልሼ አባል ሆንኩኝ፡፡ ማኅበሩ የኦሮሞዎች ማኅበር በአውሮፓ ተባለ፡፡ ይኼኛው ማኅበር የኦነግ አባል አልነበረም፡፡

ሪፖርተር፡- እርስዎ የኦነግ አባል ሆነው ከደጋፊ ማኅበሩ ጋር በመሆን ሲደግፉ ነበር፡፡ ከአባልነቱ ከወጡ በኋላ አዲስ በተቋቋመው የሁለቱ ማኅበሮች ቅልቅል ውስጥ ተመልሰው አባል ሆኑ፡፡ ማኅበሩ ሥራው ምን ነበር? የምትረዱት ወይም የምትወክሉት የትኛውን የፖለቲካ ድርጅት ነበር?

ዶ/ር ነጋሶ፡- የማኅበሩ ዋና ዓላማ ኦሮሞዎችን ለማስተማር፣ የኦሮሞ ትግል ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ እንዲያገኝ ማድረግ፣ በየአካባቢው በሱዳን፣ በኬንያና በሶማሊያ ያሉትን ስደተኞችን መርዳት ነበር፡፡ ግን ማኅበሩ ገና በመመሥረት ላይ እያለ በ1982 ዓ.ም. በአውሮፓ ውስጥ አንድ ቡድን ተፈጠረ፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ነፃነት ድርጅት (OPLO) ተፈጠረ፡፡ የኦነግና የኦፒኤልኦ ልዩነት ነበራቸው፡፡ ኦነግ በኢትዮጵያ ስም ከተደራጁ ማኅበራት ጋር አይሠራም፡፡ ኦፒኤልኦ ግን ዴሞክራሲያዊ ከሆኑ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር እሠራለሁ ይላል፡፡ ይኼ ድርጅት ኦፒኤልኦ እንደተመሠረተ (በጀርመን) ኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ መጣ፡፡ ደርግ ተሸነፈ፡፡ በ1982 ዓ.ም. የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ተቋቋመ፡፡ የሕወሓት ወኪል (በጀርመን) ነጋሽ ተክሉ (የዋልታ መሥራች) በኩል መረጃ እናገኝ ነበር፡፡ እነካሱ ኢላላ፣ ተፈራ ዋልዋና ወረደ ጀርመን መጥተው ስለኢሕአዴግና ኦሕዴድ መቋቋም ይነግሩን ነበር፡፡ በ1983 ዓ.ም. ዘመቻዎች ተጀመሩ፡፡ የዋለልኝ ዘመቻ፣ የቴዎድሮስ ዘመቻ፣ ዱላ ወልቂጡማ ቢሉሱማ ዘመቻዎች ነበሩ፡፡ ኢሕአዴግ ከጎጃም ወደ ወለጋ መሸጋገር ሲጀምር ኦፒኤልኦና የኦሮሞዎች ማኅበር በአውሮፓ አንድ ዘመቻ ጀመሩ፡፡ ዘመቻው መቆም አለበት የሚል፡፡

ሪፖርተር፡- ለምን?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ኢሕአዴግ ወደ ኦሮሚያ መግባት የለበትም፡፡ ይኼ ዳግም ወረራ ነው፡፡ መቆም አለበት አሉ፡፡ በዚያ ወቅት ትግራይና አማራ ክልል ከደርግ ነፃ ወጥተው ነበር፡፡ የእነሱም ጥያቄ ኦሮሚያም ነፃ መሆን አለበት የሚል ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ እኔ ኢሕአዴግ ወደ ኦሮሚያ አይግባ ስትሉ በሌላ አባባል ደርግ በኦሮሚያ ይቆይ እያላችሁ ነው አልኩኝ፡፡ መርዳት አለብን፡፡ ኦሕዴድንና ኢሕአዴግን ረድተን ደርግን ማስወገድ አለብን አልኩኝ፡፡ ባለመስማማታችን ማኅበሩን ለቅቄ ወጣሁ፡፡ ግንቦት 19 ቀን 1983 ዓ.ም. ወደ ሱዳን መጣሁ፡፡

ሪፖርተር፡- እንዴትና ለምን ወደ ሱዳን ሊመጡ ቻሉ?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣትና ኦሕዴድን ለመቀላቀል፡፡

ሪፖርተር፡- ጀርመን እያሉ የኦሕዴድ አባል ሆነው ነበር እንዴ?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ቀደም ብዬ እንደገለጽኩልህ በጀርመን የኢሕአዴግ ተወካይ ከነበረው ከነጋሽ ተክሉና ከሌሎቹም ጋር ተነጋግረንና ተወያየን ተስማምተን ነበር፡፡ ቪዛ ያዘጋጀልኝና ወደ ሱዳን እንድገባ ያመቻቸልኝም ነጋሽ ተክሉ ነው፡፡ ምክንያቱም እኔ የጀርመን ዜግነት አልፈልግም ብዬ የነበረኝ የስደተኞች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ፓስፖርት ነበረኝ፡፡ ቪዛዬን ያመቻቸልኝ ኢሕአዴግ ነው፡፡ የአዲስ አበባ መያዝን የሰማሁት ሱዳን ውስጥ እያለሁ ነው፡፡ ከሱዳን ግንቦት 21 ቀን 1983 ዓ.ም. ተነስተን በጎንደር፣ በቡሬ ዳሞት አድርገን ግንቦት 23 ቀን 1983 ዓ.ም. ነቀምቴ ገባሁ፡፡ ከኦሕዴድ ጋር አንድ ወር ቆይቼ ወደ ጀርመን በመመለስ ጠቅልዬ ወደ ኢትዮጵያ ተመለስኩኝ፡፡

ሪፖርተር፡- ወደ ኢትዮጵያ ጠቅልለው ከተመለሱ በኋላ በዋናነት ሊሠሩት ወይም ሊሳተፉበት ያቀዱት ነገር ምን ነበር?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ዋና ዕቅዴ ወደ አይራ ተመልሼ ለማስተማር ነበር፡፡ ሌላ ሐሳብ አልነበረኝም፡፡ በወቅቱ ከመተማ እስከ ነቀምቴ ድረስ የነበረው አብዛኛው ሠራዊት የሕወሓት ነበር፡፡ ነቀምቴ እንደደረስኩ የኦሕዴድ ተሳትፎ በኢሕአዴግ ውስጥ ምን ያህል ነው? ከዳር እስከ ዳር የሕወሓት ሠራዊት ብቻ መታየቱ ደግሞ በአውሮፓ ‹‹ዳግም ወረራ ነው›› እየተባለ የሚወራውን የሚያረጋግጥ በመምሰሉ ለምን በሚል ጥያቄም አነሳሁ፡፡ በዚህ ወቅት ኩማ ደመቅሳ፣ አባዱላ ገመዳና ሐሰን ዓሊን ነበር ያገኘኋቸው፡፡ ስጠይቃቸው ‹‹እኛ የተመሠረትነው በቅርቡ ነው፡፡ ዓመትም አልሞላንም፡፡ እነሱ ግን ከአሥር ዓመታት በላይ ሆኗቸዋል፤›› አሉኝ፡፡ አሁን በምልመላ ራሳችንን ማጠናከር እንዳለብን ገለጹልኝና የኢሕአዴግ ሠራዊት የመጣው ክልሉን ይዞ ለመቆየት ሳይሆን የደርግ ሠራዊትን ተባብሮ ለማባረር መሆኑን ሲያስረዱኝ ተስማማሁ፡፡ እኔም መርዳት እንዳለብኝ ወስንኩኝና የኦሕዴድ አባል ሆንኩኝ፡፡ የሰላም ኮንፈረንስ በተደረገበት ወቅት ጠቅልዬ ለመምጣት ጀርመን ሄጀ ስለነበር አልተሳተፍኩኝም፡፡ ተመልሼ ስመጣ የሽግግር ፓርላማ ሲቋቋም ኦሕዴድ ከ12ቱ ወኪሎቹ አንዱ እንድሆን መረጠኝ፡፡ የሽግግር መንግሥት ተቋቋመ፡፡ በወቅቱ ታምራት ላይኔ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንድሆን ጠየቀኝ፡፡ በ1984 ዓ.ም. የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ሆኜ ተሾምኩ፡፡ በዚያ ወቅት ዲማ ነገዎ የማስታወቂያ ሚኒስትር ነበር፡፡ እሱ ሲለቅ በ1985 ዓ.ም. ወደ ማስታወቂያ ሚኒስትር ተዛወርኩኝ፡፡ የክልሎች ማቋቋሚያ ምርጫ ሲደረግ የምርጫ ኮሚሽን አባል ሆንኩኝ፡፡ እኔና ዳዊት ዮሐንስ ለሕገ መንግሥት ጉባዔ ከኢሕአዴግ ተወከልን፡፡ በ1987 ዓ.ም. ፕሬዚዳንት ሆኜ ተመረጥኩ፡፡ እስከ 1994 ዓ.ም. ድረስ ለሰባት ዓመታት ፕሬዚዳንት ሆኜ ሠራሁ፡፡

ሪፖርተር፡- ከፕሬዚዳንትነት ከለቀቁ በኋላ የፖለቲካ ተሳትፎ አቁመው ነበር፡፡ ለምን ነበር?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ከ1994 ዓ.ም. እስከ 1996 ዓ.ም. ድረስ ምንም ዓይነት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ አልነበርኩም፡፡ ማለትም ከፖለቲካ ወጥቻለሁ ወይም ምንም ዓይነት ፍላጎት አልነበረኝም ሳይሆን፣ በማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ አልነበርኩም ማለቴ ነው፡፡ በ1997 ዓ.ም. ደንቢዶሎ በመሄድ በግል ተወዳድሬ ፓርላማ ገባሁ፡፡ እስከ 2002 ዓ.ም. ድረስ በፓርላማ ስሳተፍ ቆይቻለሁ፡፡ ፓርላማ ውስጥ እያለሁ ከእነአቶ ቡልቻ ደመቅሳ፣ ተመስገን ዘውዴ፣ መረራ ጉዲና፣ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ጋር በመወያየት ‹‹ለምን ፓርቲዎቹ አብረው አይሠሩም?›› የሚል ምክክር ጀመርን፡፡ በመቀጠልም መድረክን አቋቋምን፡፡ ወደ ጥምረት ሲሸጋገርና በምርጫ ቦርድ ሲመዘገብ እኔ የግዴታ የአንድ ፓርቲ አባል መሆን ነበረብኝ፡፡ በወቅቱ ከነበሩት ፓርቲዎች የትኛው እንደሚሻለኝ ለመምረጥ ፕሮግራማቸውን ወስጄ አጠናሁ፡፡ የተሻለ ፕሮግራም ያለውና ለእኔ ምርጫ የተስማማኝ አንድነት በመሆኑ የአንድነት አባል ሆንኩኝ፡፡

ሪፖርተር፡- አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲን (አንድነት) ሲቀላቀሉ ‹‹አሁን ገና ለሕዝብ የሚሠራና ከሕዝብ ጋር የሚያገናኝ ፓርቲ አባል ሆንኩኝ፡፡ በዚህም በጣም ደስተኛ ነኝ፤›› ብለው ነበር፡፡ አሁንም እንደነገሩኝ ጥሩ ፕሮግራም ያለውና በወቅቱ ለእኔ ምርጫ የተስማማ ፓርቲ ያገኘሁት አንድነትን ነበር ሲሉኝ፣ ሲቀላቀሉ ባደረጉት ንግግር ላይ ያሉትን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ከአምስት ዓመታት ቆይታ በኋላ በመካከላችሁ ምን ገብቶ ለመለያየት በቃችሁ?

ዶ/ር ነጋሶ፡- ያንን ማለቴን አሁን አላስታውስ&

ምንሊክ ሳልሳዊ በአዲስ አበባ ውስጥ የሚገኙ ከፍተኛ የሆኑ የብኣዴን እና የኦሕዴድ ከፍተኛ ባለስልጣናት መቀራረብ እና አብሮ መዋል የሕወሓት ሰዎችን ማሳሰቡን እና የደህንነት ክትትል እያደረጉባቸው መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል:: ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከደመቀ መኮንን እና ከሙክታር ከድር ጀምሮ እስከ በታች የፌዴራል ባለስልጣኖች ላይ ከፍተኛ ስለላ እየተካሄደ መሆኑን ታውቋል::

ሃገሪቱ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሳለች ከፊታችን አደጋ ተደቅኗል::የሚሉ የተቆጡ ድምጾች በስፋት በእሕኣዴግ አባላት እየተሰሙ ያለበት አጣብቂኝ ውስጥ የከተተው ሕወሓት በግል እና በጋራ ባለስልጣናቱ ላይ ከፍተኛ ማስፈራራት እና ዛቻ እያደረገባቸው መሆኑን የተናገሩት ምንጮቹ ኢሓዴግን ለመናድ ብትሞክሩ ሃገሪቷ ትበታተናለች ;እንደ ሱማሊያ መንግስት አልባ ሆና ትበጠበጣለች እያሉ ከማስፈራራትም አልፎ በግል የተነከራችሁበት ሙስና አደባባይ እናወጣዋለን:: እኛን ማንም ሊተይቀን አይችልም ቁልፉ እኛ ጋር ነው የሚሉ በኣደገኛ መርዞች የተሞሉ ማስፈራሪያዎች በመሰንዘር ላይ ናቸው ሲሉ ምንጮቹ ተናግረዋል::

የብኣዴን እና የኦሕዴድ ባለስልጣናት የየቀን ሪፖርት እና ግንኙነት በተመለከተ ማን ከማን ጋር እንደዋለ ማን እነማን ቤት እንደሄደ በመከታተል እየቀረበ ሲሆን የሃገሪቱን የደህንነት ቢሮ በጋራ የሚመሩት አቶ ጸጋዬ አቶ ጌታቸው እና ዶ/ር ደብረጺሆን በየቀቱ ለትግሪኛ ተናጋሪ ደህንነቶች በአጫጭር ስብሰባዎች መመሪያ እያወረዱ ከመሆኦኑም በላይ አደጋ ውስጥ መሆናቸውን እየደጋገሙ እንደሚናገሩ ምንጮቹ አክለዋል::

ይህ በእንዲህ እንዳለ ከዚህ ቀደም በእሕዴድ ወጣቶች የተጀመረው እና የሌንጮ ለታ ወደ አገር ቤት የሚለውን ዜማ ተከትሎ የለውጥ ጥያቄ እያንሰራራ መሆኑ ታውቋል:: በዚህም ምክንያት የኢሕኣዴግ አጋር ድርጅት የሆነው ኦሕዴድ ወጣት አባላት እና ለውጥ ፈላጊዎች ራሳቸውን ውስጥ ውስጡን እያደራጁ ነው በሚል ሕወሓት የድርጅቱን መዋቅር ሊበርዘው መሆኑ ተሰምቷል:: በተለያዩ ፖለቲከኞች ዘንድ ኦሕዴዶች ድምጻቸውን አጥፍተዋል እየተባለ ባለበት በዚህ ወቅት ሕወሓት አሳሳቢ ጉዳይ ላይ ነው ሲል ይነጋገርበት ጀምሯል::

በወጣቶቹ የኦሕዴድ አባላት መሃከል በተፈጠሩ መግባባቶች እስከመቼ ድረስ የፖለቲካ አሽከር ሆነን እንቀጥላለን የሚሉ የድርጅቱ ካድሬዎች በዙሪያቸው እየተቧደኑ ሲሆን ይህ ያሰጋው ሕወሓት የእነዚህ ሰዎች ዝምታ ይህን ሰሞን በአመራሮቹ ደረጃ በቢሮ ስብሰባ እየተነጋገረበት ይገኛል::

ጥርሳቸውን ነክሰው አድፍጠው ያሉት የኦሕዴድ አባላት በስልጣን ክፍፍሉ እና ራሳችንን መምራት ያለብን ራሳችን ነን በሚል እንዲሁም በተያያዥ የፖለቲካ ጉዳዮች በተጨማሪም በኦሮሚያ ክልል ያሉት የህዝብ ሃብቶች ላይ የሕወሓት ባለስልጣናት የሚሰጡት ውሳኔ እንደፖለቲካ ባርነት ነው የሚሉ ሮሮዎች በመደመጥ ላይ ሲሆኑ ነጻነታችንን መረጋገጥ አለብን የሚሉ ቢሊሶማ2 የተሰኙ ወጣት ባለስልጣናት ሕወሓትን አጣብቂኝ ውስጥ ከተውታል::ምንሊክ ሳልሳዊ

እንደምን ከረማችሁ?

መረጃ 1

ኦሮሞ ፈርስት በሚል ጃዋርና ሸሪኮቹ የከፈቱት ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ሰንበቴ ቤትን በተመለከተ ከዚያው መንደር የደረሰኝ መረጃ ነው። ይህ ማህበር ከመቋቋሙ በፊት ጃዋር ያላንኳኳው በር; ያልረገጠው ደጃፍ የለም። ጃዋር የቢዝነስ ጭንቅላት ያለው ይመስላል። ነጋዴ ነገር ነው። ገንዘብ እንዴት እንደሚገኝ ያውቅበታል። በአቋራጭ እንዴት መበልጸግ እንደሚችል ቀን ከሌሊት ያውጠነጥናል። በእርግጥ ኦሮሞ ፈርስት ጥሩ ብልሃት ናት። የሀረሩ አብዲ ሙተቂ እንጋለጠው ጃዋር ኦሮሞ ፈርስት የተሰኘውን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ለማቋቋም ደጅ ከጠኑት ሰዎች አንዱ አፈንዲ ሙተቂ ነው። አፈንዲ እንዲህ ዓይነቱ ጸበል ቅመሱ አላማረውም። የጃዋር የገንዘብ ስግብግብነት መጨረሻው ከወዴት እንደሆነ በጠዋቱ ነው የተገለጠለት። የኦሮሞን ህዝብ ትግል ለጨረታ ያቀረበው ጃዋር እንደ በግ ነጋዴ የኦነግን የከሰረ ፕሮጀክት ተሸክሞ ገበያ ወጣ። ፖለቲካ የምግብ ዓይነት ይሁን የኳስ ክለብ ምን እንደሆነ በውል ያላወቁ ጥቂት አክራሪዎችን ከጎኑ አሰልፎ ጃዋር ኦሮሞ ፈርስትን አስመረቀ።

ጃዋር ጥሩ የገቢ ምንጭ አግኝቷል። ኒውዮርክ ከአንድ አፓርታማ ተሸጎጦ ጫቱን እያመነዥገ፡ ጥላቻ የሚረጭበትን ዓላማ ከዳር ለማድረስ የከፈተው ፕሮጀክት እያስገኘለት ያለው ገቢ ቀላል የሚባል አይደለም። በአንድ የኦሮሞ ፈርስት መድረክ 2ሺህ ዶላር ይከፈለዋል። ይሄ የተጣራው ኪሱ የሚገባው ነው። ከለንደኑ የኦሮሞ ፈርስት መድረክ የጀመረ ደግሞ ሚስቱንም አስገብቷታል። እሷም እንደ አንድ ፓናሊስት ትቀርባለች በሚል ጃዋር የቢዝነስ አድማሱን አስፍቷል። እናም በየኦሮሞ ፈርስት መድረክ ጃዋር ሚስቱን እያንጠለጠለ ይጓዛል። በዚህም እነ ጃዋር ቤት በአንድ የኦሮሞ ፈርስት መድረክ 4ሺህ ዶላር ይገባል። ከዚህ በላይ ቢዝነስ የት ነው ያለው?

በነገራችን ላይ ሚስቱ አርፋሴ የኢትዮጵያን ምድር ረግጣ አታውቅም። ወላጆቿ ኬኒያ የሚኖሩ እዚያው ኬኒያ የወለዷት የኦሮሞ ኢትዮጵያውያን ናቸው። አርፋሴ የኢትዮጵያን አፈር አታውቃትም። ኬኒያ ተወለደች፡ እዚያው ቆየች፡ አሜሪካ መጣች። ጃዋር ከአክራሪም ጽንፈኛ የሆነው በእሷ ምክንያት እንደሆነ ይነገራል። አርፋሴ ደሟ ውስጥ የተቀበረ የኢትዮጵያ ጥላቻ እንዳላት የቅርብ መረጃዎች ያሳያሉ። አንድ ጊዜ በኒውዮርክ የሆነ ዓለም አቀፍ ፌስቲቫል ተካሄደ አሉ። የሁሉም ሀገራት ተወላጆች በፌስቲቫሉ ላይ የየሀገራቸውን ባንዲራ ይዘው በመቆም ለጎብኚዎች ስለመጡበት ሀገር ያስተዋውቃሉ። አርፋሴ የኦነግን ባንዲራ ይዛ ከመሀል ቆማለች። ጎብኚዎች ይጠጓትና ይጠይቋታል።

‘’የት ነው ይሄ ሀገር’’

‘’ኦሮሚያ ‘’ አርፋሴ ስትናገር ሀፍረት የሚባል ነገር የለም። ፈርጠም ብላ ነው የምትናገረው

‘’ኦሮሚያ የት ነው ያለው?’’

‘’…ከሶማሊያ ጎን….. ከአቢሲኒያ በታች፡…… ከኬኒያ በላይ….ሱዳን እግር ስር…..’’ አርፋሴ የትኛውን የዓለም ካርታ እያነበበች እንደሆነ ከሷ በቀር ማንም አያውቅም። ፈረንጆቹ ግራ ገባቸው።

ካርታ አውጥተው

‘’ኦሮሚያ የሚባል ሀገር እዚህ ካርታ ላይ የለም’’ ይሏታል። አርፋሴ የሌባ ዓይነ ደረቅ አይደለች?!

የማይነበብ ለእሷ እንጂ ለሌሎች የማይታየውን በመንግስታቱ ድርጅት የማይታወቀውን በእሷና በመሰሎቿ ምናብ ውስጥ የሳሏትን ኦሮሚያ የምትባል ሀገር ፈጥረው አደባባይ የወጡበትን የቅዥት ታሪክ ለፈረንጆችም ሊነግሩ ተነስተዋል። ፈረንጆቹ ግራ ገባቸው። ትተዋት ሄዱ። መቼም እብድ ናት ሳይሉ አይቀሩም።

ሴት የላከው ሞት አይፈራም። አርፋሴ ጃዋርን ጃስ ትለዋለች። ‘’ሉቡ ኪያ!’’ ስትለውማ ጃዋር ሜንጫ ፍለጋ አይኑ ይማትራል። ባልና ሚስት ከአንድ ወንዝ ይቀዳል ቢባል ከአርፋሴና ጃዋር በልጦ ምስክር የሚሆን ከየት ይገኝ ይሆን?

አሁን አርፋሴ ቢዝነስ ላይ ናት። ከባሏ ጋር 4ሺህ ዶላር በአንድ ስብሰባ እያፈሰች ናት። በ1ወር ሁለት የኦሮሞ ፈርስት መድረኮች ከተዘጋጁ እነጃዋር ቤት 8ሺህ ዶላር በወር ይገባል። በአመት ከ80ሺህ ዶላር በላይ። አሜሪካውያን 80k የሚሉት።

መረጃ 2

ጃዋር በስመጥሩ የስታንፈርድ ተቋም የስኮላር ሺፕ ትምህርቱን ተከታትሏል። መቼም ስታንፈርድ የተማረ አይደለም በአጠገቡ የተጠጋ የሚኖረው የእውቀት ደረጃ፡ ከአሁኗ ዓለም ጋር የሚፈጥረው ትስስር፡ በቀላሉ የሚገለጽ አይደለም። ከራስ ጥረት በተጨማሪ ዕድልንም ይጠይቃል ስታንፈርድ ለመግባት። ጃዋር ይሄን እድል አግኝቷል። ትምህርቱንም አጠናቆ ወጥቷል። ይሄ በአደባባይ የሚታወቅ ዕውነታ ነው። ውስጡን ለቄስ ይላሉ አበው ሲተርቱ?! ጃዋር ከስታንፈርድ የተመረቀው በአካለ ስንኩል ደረጃ (disability status) ነው ቢባል አሁን ማን ያምናል?

አዎን! ሀቁ ከወዲህ ነው ያለው።ጃዋር ከጥይቶቹ የስታንፈርድ ተማሪዎች ጋር የሚፎካከርበት አቅም አልነበረውም። ለነገሩ ማንም ሰው እንዲሁም መገመት የሚችል ይመስለኛል። ገና ከመንደር የጎሳ ጭንቅላት ያልተላቀቀ ወጠጤ፡ ዓለምን ገልብጠውና ተልትለው ከሚረዱት ምጡቅ ተማሪዎች ጋር ተፎካክሮ ይወጣል ማለት የማይታሰብ ነው። እናም ጓድ ጃዋር መውጪያ ቀዳዳ ፍለጋ ብልሃት መጣለት። በኤትዮጵያ እያለ በደል ይደርስበት፡ ስቃይና መከራ ይፈራረቁበት እንደነበረ፡ ህይወቱን በሙሉ መንግስትና የአማራው ገዢ መደብ እንደሚያሰቃዩት በመዘርዘር የአይምሮ ጉዳት እንደገጠመው፡ ይህም በትምህርት የመቀበል አቅሙ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዳደረሰበት በመተረክ ደብዳቤ ያስገባል። የስታንፈርድ ተቋምም ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ ጃዋር ከሌሎች ተማሪዎች ጋር በእኩል ደረጃ መመዘን የለበትም የሚል ውሳኔ ያስተላልፍና የተለየ ድጋፍ እንዲደረግለት ያዛል። ጃዋር የአካለጎዶሎ መብት ተሰጠው። በቃ! ፈተና ላይ የሚሰጠው ጊዜ ከሌሎቹ ተማሪዎች በእጥፍ የበለጠ ነው። በውጤት ደረጃም የጃዋር የማለፊያ ነጥብና የሌሎቹ የተለያየ ነው። በዚህ መልኩ ነው እንግዲህ ጃዋር ከስታንፈርድ የተመረቀው።

የደህንነት መስሪያ ቤት ዘመቻ

የወያኔ የደህንነት መስሪያ ቤት የወያኔ ዕድሜ ለማራዘም ከሰማይ በታች ያለውን ማንኛውንም እርምጃ ለመውሰድ ተዘጋጅቷል። በዚህም የተለያዩ ዘመቻዎችን ከፍቷል። ምንጮች እንዳረጋገጡት እነጃዋር በሚኒሊክ ላይ የከፈቱት ዘመቻ የዚሁ የደህንነት መስሪያ ቤት ዕቅድ አንዱ አካል ነው። እነጃዋር ከወያኔ ጋር ጋብቻ ለመፈጸማቸው ማረጋገጫው ሆኖ ተወስዷል። ባለፈው የሀረሩ አፈንዲ ሙተቂ እንደጻፈው ጃዋር ከወያኔ ጋር ይሰራል። ምናልባት የሙተቂን ሀሳብ እብዳለ እዚህ ላስቀምጠው።

‘’ይህ ሰው በጣም አጭበርባሪ ነው፡፡ የውሸት ወሬ መፈብረክ ይችልበታል፡፡ ደግነቱ የሚፈበርካቸውን ወሬዎች ሀሠትነት ለማረጋገጥ ረጅም ጊዜ አይፈጅም፡፡ የዚህ ሰው ሌላኛው ባህሪ ደግሞ ለሁሉም የፖለቲካ ቡድኖችና ፓርቲዎች የሚሰራ መሆኑ ነው፡፡ ሰውዬው ከላይ ሲታይ የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚ ይመስላል፡፡ ሆኖም አብዛኛው ሰው እንደሚያውቀው ከኦፒዲኦ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋርም የጠበቀ ግንኙነት አለው፡፡ አንድ ቀን ሳያስበው ይህንን ግንኙነቱን ግልጽ ያደረገበትን ጥያቄ ጠየቀኝ፡፡ እኔ በሰጠሁት ምላሽ ሳስደነግጠው ትንሽ እንደማፈር ብሎ ዘጋው (በወቅቱ የጠየቀኝን ጥያቄ ሌላ ጊዜ ብነግራችሁ ይሻላል)፡፡ በርሱ ቤት ነገሩን የማላውቅ መስሎታል፡፡ ይሁንና በፌስቡክም ጭምር በሰፊው ሲባል የነበረ ነገር በመሆኑ ብዙም አልደነቀኝም፡፡’’

የጃዋርንና የወያኔን ጋብቻ በተመለከተ ከዚህ በፊት ብዙ ስላልኩበት አሁን አልመለስበትም። አፈንዲ የተናገረው ከበቂም በላይ ነው። እንደዚህ ያለ ምስክርነት ለጃዋር የአደጋ ምልክት ነው። ጃዋር የወያኔ ጉዳይ አስፈጻሚ ስለመሆኑ የማያምን ካለ እሱ ወይ ራሱ ወያኔ ነው አልያም ሳያላምጡ ከሚውጡት ጃዋራውያን አንዱ ነው ወይም ደግሞ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም አይነት ነገር ነው።

ከደህንነት መስሪያ ቤት አከባቢ የተገኘው መረጃ እንደሚያረጋግጠው ገና በርካታ ህዝብን ከህዝብ የሚያጋጩ ዘመቻዎች በወያኔ በኩል ይከፈታሉ። የእነጃዋር ቢባርቅም በተወሰነ ደረጃ የተንጠባጠቡትን ለቃቅመሞ ውዥንብርና ጫጫታ ለመፍጠር መሞከሩ የሚጠበቅ ነው። በእርግጥ የእነጃዋር ጫጫታ ከፌስ ቡክ መንደር ብዙም ርቀት መሄድ አልቻለም። የጃዋር ተከታዮች ልጆቻቸውን እዚህ በእንግሊዘኛ እያስተማሩ ኦሮምኛ ቋንቋ በልጆቻቸው አፍ ዝር እንዳይል እየተከላከሉ፡ ሀገር ቤት ያሉትን ምስኪኖች የቁቤ ትውልድ በተሰኘች መሸንገያ ከኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር ደም ለማቃባት መፍጨርጨራቸው በቀጣይም የሚጠበቅ ነው። ለዚህም የወያኔ የደህንነት መስሪያ ቤት መዋቅር ዘርግቶ እየሰራበት ነው።

የቀቢጸ ተስፋው ዘመቻ

አሁን ጫጫታው በርዷል። 21ኛው ክፍለ ዘመንን ያረከሱት እነጃዋር ጥጋቸውን ይዘው የመከላከል ስትራቴጂን የሙጥኝ ብለዋል። የተኮሱት ጥይት ዞሮ እነሱ ላይ እየተምዘገዘገ ነው። ባርቆባቸዋል። ለ40 ዓመት ኦነግን በርስትነት ይዘው የቆዩት እነ ሌንጮ ለታ ወደ ሀገር ቤት እንገባለን ብለው ማወጃቸው ለነጃዋር ግራ የሚያጋባ ሆኗል። ኦህዴድን ከኦነግ ጋር በመቀየጥ ወይም በማጋባት አዲስ ጽንፈኛ የኦሮሞ ድርጅት ለመፍጠር ከወያኔ ጋር እየሰራ ላለው ጃዋር የእነ ሌንጮ ለታ ወደ ሀገር ቤት እንገባለን ዜና አስደንጋጭ ነው። ወያኔ ምን እያደረገ ነው? ለጃዋር ጥሩ ጊዜ ከፊት እየመጣ አይመስልም። ወያኔ ጊዜያዊ የፖለቲካ ትርፍ እያሰላ የሚንቀሳቀስ ማፊያ ድርጅት መሆኑን ጃዋር በእርግጥ አያውቅም ማለት ይከብዳል። ለነገሩ በአካለ ጎዶሎ መብት ለተመረቀ ወጠጤ አእምሮ ውስብስቡ የወያኔ ሴራ የሚከብደው ይመስላል።

አሁን ነገሮች ውል እየያዙ ነው። ጃዋርን ለፍርድ ለማቅረብ የተጀመረው ዘመቻ ተቀጣጥሏል። የህግ ባለሙያዎች እንዳረጋገጡት ጃዋርን ለዘር ማጥፋት ወንጀል ቅሰቀሳ በማድረግ በሚለው ክስ ችሎት ለመገተር የሚያስችሉ በቂ የድምጽ፡ የቪዲዮ እና የጽሁፍ ማስረጃዎች አሉ። የሚቀረው ፊርማ አሰባስቦ ለሚመለከተው አካል ማቅረብ ነው። ያም እየተሰራበት ነው። በሌላ በኩል በሰለጠነው የምዕራቡ ኣለም እየኖሩ ኢትዮጵያውያን ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲፈጸም በሚቀሰቅሱት ጽንፈኛ ኦሮሞች ላይ የሚከፈተው ክስን በተመለከተ የህግ ምሁራን እየመከሩበት ሲሆን ጉዳዩ ከተጀመረ ለእነጃዋርና መንጋዎቹ መጪው ጊዜ በጨለማ የተጋረደ እነደሆነ እየተነገረ ነው።

እናም የቀቢጸ ተስፋ እርምጃዎች በጃዋርና መንጋዎቹ በኩል እየተካሄደ ነው። ምን ያህል ርቀት ይወስዳቸው ይሆን? የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በቀር በቅርቡ የሚረጋገጥ ይሆናል።

http://ecadforum.com/

“ኦክስፋም” በመልካም ሥራቸው ከታወቁ ትላልቅ ዓለም ዓቀፍ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አንዱ ነው። በቅርቡ አንድ መቶ ሀያ አምስት አገሮችን ያካተተ ከምግብ አቅርቦትና አጠቃቀም ጋር የተያያዘ ጥናት ውጤት ይፋ አድርጓል። ጥናቱ አራት ዝርዝርና አንድ አጠቃላይ አመላካቾች አሉት።

1. አመላካች አንድ: የምግብ እጥረት

ይህ አመላካች “በየአገሮቹ ምን ያህል ለበላተኛው የሚበቃ ምግብ አለ?” የሚለውን ይለካል። በጥናቱ ውጤት መሠረት በምግብ እጥረት እጅግ የተጎዱ የመጨረሻዎቹ አስር አገሮች የሚከተሉት ናቸው: – ቡሩንዲ፣ የመን፣ ቻድ፣ ኢትዮጵያ፣ ማዳጋስካር፣ ናይጄሪያ፣ ላኦስ፣ ባንግላዴሽ፣ መካከለኛዉ አፍሪካ ሪፑብሊክ እና ህንድ። ኢትዮጵያ አገራችን ከመጨረሻ አራተኛ ናት።

2. አመላካች ሁለት: ለምግብ የመክፈል አቅም (Affordability)

ይህ አመላካች “የአገሩ ሕዝብ በአገሩ ዋጋ ምግብ ገዝቶ ለመብላት ምን ያህል አቅሙ ይፈቅድለታል?” የሚለውን የሚመልስ ነው። አሁንም ከመጨረሻ እንጀምር። አንጎላ፣ ዚምባቡዌ፣ ቻድ፣ ጉያና፣ ኢትዮጵያ፣ ናይጄሪያ፣ ኮንጎ፣ ኬንያ፣ ጋምቢያ እና ኢራን የየአገሩ ሕዝብ ምግብ መሸመት የሚቸገሩባቸው አገሮች ናቸው። አገራችን ኢትዮጵያ ከመጨረሻ አምስተኛ ናት።

3. አመላካች ሶስት: የምግብ ጥራት

ይህ የምግብ ይዘትንና የአያያዝ ንጽህናን የሚመለከት ሲሆን ኢትዮጵያ፣ ማዳጋስካር፣ሞዛምቢክ፣ ቻድ፣ ቶጎ፣ ዛምቢያ፣ ማሊ፣ ናይጄሪያ፣ ባንግላዴሽ፣ ሌሶቶ ከመጨረሻው እስከ አስረኛ ደረጃ ይዘዋል። ኢትዮጵያ በምግብ ጥራት የመጨረሻዋ አገር ናት።

4. አመላካች አራት፡ የሰውነት ውፍረት እና የስኳር በሽታ

ይህ አመላካች ከልክ ያለፈ ውፍረት ዓለም ዓቀፍ የጤና ችግር እየሆነ በመምጣቱ የገባ አመልካች ነው። ኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥሩ ውጤት ያመጣችሁ በዚህ አመላካች ብቻ ነው። ኢትዮጵያ አብዛኛው ሕዝቧ ቀጫጫ ነው፤ የስኳር በሽታም እንደሌላው አገር የተስፋፋባት አገር አይደለችም።

5. አማካይ ውጤት

የእነዚህ አራት አመላካቾች ድምር ውጤት አጠቃላይ ውጤትን ይሰጣል። በአጠቃላይ ውጤት: ቻድ፣ ኢትዮጵያ፣ አንጎላ፣ ማዳካስካር፣ የመን፣ ቡሩንዲ ናይጄሪያ፣ ሞዛምቢክ፣ ዚምባቡዌ፣ ሴራሊዮን ከመጨረሻ እስከ አስረኛ ወጥተዋል። ኢትዮጵያ ከመጨረሻ ሁለተኛ ነች።

ይህ ምንን ያመለክታል?

ወያኔ ባለፉት አስር ዓመታት በተከታታይ ከ11% በላይ ኢኮኖሚውን አሳድጌዋለሁ ሲለን ነበር። እድገቱ ያተኮረው ገጠር፤ ምንጩም ግብርና ነው ብሎን ነበር። ሐቁ ግን ከላይ የተመለከተው ነው።

እርግጥ ነው የወያኔ ሹማምንት በከተሞች ሕንፃዎችን ይገነባሉ፤ በገጠሮች በመቶዎች ሄክታር የሚለካ ለም መሬት ይዘው ፈጣን ገንዘብ በሚያስገኙ የአበባ፣ የጫትና የቃጫ ምርት ላይ ተሰማርተዋል። ከራሳቸውም አልፈው ሀብታም የውጭ አገራት ሸሪኮቻቸውን በአገራችን ለም መሬት ይበልጥ ያበለፅጓቸዋል። የእነሱ የግላቸው፣ የቤተሰቦቻቸው፣ የዘመዶቻቸው እና የሸሪኮቻቸው ኢኮኖሚ እየተመነደገ መሆኑን እናውቃለን። ይህን በገዛ ዓይኖቻችን የምናየው ሀቅ ነው።

ሆኖም ግን የእነሱ ኢኮኖሚ ማደግ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ማደግ አለመሆኑ እናውቃለን። አገራችን ከጓረቤት አገሮች ጋር ስትነፃፀር ወደ ኋላ እየቀረች መሆኑ ያንገበግበናል። በቅርቡ አክስፋም በጥናት ያረጋገጠዉ የኢትዮጵያ ገበሬዎች በየቤታቸው ከወዳጆቻቸው ጋር በምስጢር የሚያወሩትን እውነት ነው።

ከሳምንት በፊት ደግሞ “ኢኮኖሚክ ኢንተለጀንስ ዩኒት” የተሰኘው ታዋቂ የምርምር ተቋም አንድ የጥናት ውጤት ይፋ አድርጎ ነበር። በዚህ የጥናት ውጤት መሠረት በዓለም በከፍተኛ ፍጥነት እያደጉ ያሉ አስር አገሮች በቅደም ተከተል ሞንጎሊያ፣ ሴራሊዮን፣ ቱርክሜንስታን፣ ቡታን፣ ሊቢያ፣ ኢራቅ፣ ላኦስ፣ ቲሞር-ሊስቲ፣ ኤርትራ እና ዛምቢያ ናቸው። በዝርዝሩ ውስጥ ኢትዮጵያ አገራችን የለችበትም።

በዓለም አቀፍ መድረኮችም የወያኔ መረጃዎች ውሸትነት እየተጋለጡ መሆናቸው በጎ ምልክት ነው። የሚያሳዝነው ግን ይህንን ሀቅ የሚያዉቁ ምዕራባዉያን ለጋሽ አገሮች አሁንም ወያኔን እየረዱና እየደገፉ ሥቃያችን የሚያራዝሙብን መሆኑ ነው።

ለዚህም ነው ግንቦት 7፡ የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ዘላቂ መፍትሔ ሊመጣ የሚችለው በአገራችን መሠረዊ የሆነ የአስተዳደር ለውጥ ሲኖር ነው ብሎ የሚያምነው። የወያኔ አገዛዝ በዲሞክራሲያዊ አስተዳደር እስካልተተካ ድረስ የኢትዮጵያ አብዛኛው ሕዝብ መደህየቱ፤ ጥቂት ሀብታሞች ደግሞ በብዙሀኑ ድህነት መበልፀጋቸው አይቀርም። የወያኔ ውሸቶች ለኢትዮጵያ ድሀ ምግብና መጠለያ አይሆኑለትም። ለኢትዮጵያ ዘላቂ ጥቅም ማምጣት የምንችለው ወያኔን አስወግደን በምትኩ ለሕዝብ ሁለተናዊ እድገት የሚጨነቅ መንግሥት መምረጥ ስንችል ብቻ ነው።

ስለሆነም ግንቦት 7፡ የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በውሸት እድገት እያደናቆረን፤ በተግባር ግን እያደኸየን ያለውን ዘራፊውን ወያኔን አስወግደን በሕዝብ ነፃ ምርጫ የተመረጠ መንግሥት እንዲኖረን ትግላችን እናጠንክር ይላል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

የጀመርነው ህዝባዊ ንቅናቄ ለትግሉ ፅናታችንን፣ ለወኪሎቻችን ታማኝነታችንን ማረጋገጫ ነው!
እሁድ ጥር 18/2006

በ ‹‹730 ቀናት ለሃይማኖት ነፃነት›› ህዝባዊ ንቅናቄ ጅማሮ በሃገራችን አራቱም አቅጣጫ የሰላማዊ ትግላችን ማዕከላት የሆኑት መስጂዶች እንደትግሉ ጅማሮ ወኔ በታጠቁ አማኞች ዙሪያቸው ተጥለቅልቆ ነበር፡፡ የትናንት ወዲያው ጁሙዓ በ2004 በረመዳን ዋዜማ እንደነበሩት ግዙፍ ድምፅ አልባ ተቃውሞዎች ታለቅ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡

በአሁኑ ጁሙዓ እና በረመዳን ዋዜማ የነበሩቱን አንድ የሚያደርጓቸው ወሳኝ ነጥቦች አሉ፡፡ የረመዳኑ ዋዜማ አስደማሚ ድምፅ አልባ ተቃውሞዎች መንግስት ሰላማዊ ትግላችንን ለወራት ባወደሰበት ሚዲያው እና ባለስልጣናቱ ‹‹የሽብር እንቅስቃሴ›› ሲል የሀሰት ስም የለጠፈበት፣ ኮሚቴዎቻችንን የማሰር ፖለቲካዊ ውሳኔ ተላልፎ ከፍተኛ ውጥረት የነገሰበትና የኮሚቴዎቻችን መታሰርም እውን እንደሚሆን ሁሉም የተረዳበት፣ ህጋዊ ወኪሎቻችን በማንኛውም ቅፅበት እጃቸውን ለካቴና፣ ወገባቸውን ለበዳዮች ዱላ እያመቻቹ እኛን ግን በፅናት እና በሰላማዊነት ላይ ‹‹አደራ! አደራ!›› ያሉብን ታሪካዊ ወቅት ነበር፡፡ ትግላችንም እኛም በፅኑ የምንፈተንበት ጊዜ ነበር፡፡ የህዝበ ሙስሊሙ የወቅቱ ጀግንነት እና ወኔ ይህንን ፈተና በሚገባ ተሻግሮ ትግሉን ለማስቀጠል ትልቅ ዋስትና የሰጠ ነበር፡፡ በእርግጥም የሁለት አመት ትግላችንን በምናስብበት በዚህ ወቅት በዚያ የረመዳን ዋዜማ ላይ በአስደናቂ ህዝባዊ ወኔ የተሳተፉ ሁሉ ተገቢውን ክብር ሊቸራቸው ይገባል፡፡

አሁን የምናደርገው ህዝባዊ ንቅናቄ ደግሞ መንግስት ‹‹በእምነቴ ጣልቃ አትግባ!›› ስላለ ብቻ መላው ሙስሊም ላይ እንዳሻው በሚዘውረው ፍርድ ቤቱ ‹‹ሽብርተኛ›› ሲል የጥፋተኝነት ውሳኔ ባስተላለፈበት ማግስት የሚካሄድ ነው፡፡ ውድ ኮሚቴዎቻችንም ለወራት የደረሰባቸውን ግፍ እና መከራ ቃል በቃል በመግለጫቸው አስተላልፈውልናል፡፡ ከዚህ በኋላ የሚተላለፍባቸው የፖለቲካ ውሳኔ ምን እንደሆነ ሳያስጨንቃቸው በዚህ ስቃይ ውስጥ አልፈው፣ ፅናት ተላብሰው በፅናት እና ሰላማዊነት ላይ የጠበቀ አደራ በመግለጫቸው አስተላልፈውልናል፡፡ የጁሙዓው ሃገር አቀፍ ንቅናቄ እና አለም አቀፍ መርሃ ግብሮች ለሰላማዊ ትግላችን ያለን ፅናት እና ለወኪሎቻችንን ያለን ታማኝነት ዳግም የተረጋገጠበት ሌላ ታሪካዊ ወቅት ነው፡፡ አሁንም በዚህ ወሳኝ ወቅት ለትግሉ ባለቤት መላው ኢትዮጵያዊ ሙስሊም ክብር ሊቸረው ይገባል፡፡

በእርግጥ ህዝበ ሙስሊሙ ለሰላማዊ ትግሉ ያለው ቁርጠኝነት ፈፅሞ የሚያጠራጥር አይደለም፡፡ ነገር ግን በትናንቱ ጁሙዓ ድምፅ አልባነቱን ጥሶ የተስተጋባው ትልቁ መልእክት መጪው ጊዜ ካለፉት የተሻለ አንድነት የሚጠይቅ እና ከመቼውም የበለጠ ለድል የቀረበ እንደሆነ ነው፡፡ በሰላማዊ ትግል ውስጥ ህዝቡ ሊያልፍባቸው የሚገቡ እርከኖችን በሙሉ እየተሻገረ በመጣ ቁጥር የመጨረሻው የድል በር ላይ ለመድረሱ ማረጋገጫ መሆኑ ነው፡፡ በሰላማውያን እና ሰላማዊነት በማይዋጥላቸው አካላት መካከል ያለው ትልቁ ልዩነት ይህ ነው፡፡ ሰላማውያን ከእነርሱ የሚጠበቀውን ሁሉ እያሟሉ በማለፋቸው እና ረጅም ርቀት በመጓዛቸው ለድላቸው ፍሬ ይበልጥ መብሰል ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር እንደሆነ ያምናሉ፡፡ በተቃራኒው ያሉ አካላት ሰላማዊ የመብት ታጋዮች የሚያልፏቸውን የትግል እርከኖች ያመከኑ ሲመስላቸው ታጋዮችን ሌላ መፈናፈኛ እያሳጡ እንደሆነ ያስባሉ፡፡ የሰላማዊ ትግል ሂደት መራዘምም ‹‹ታጋዮችን ከመንገድ ያስቀራል›› ብለው ያስባሉ፡፡ የትናንቱ ጁሙዓ ህዝባዊ ወኔ ይህንን ደካማ አስተሳሰብ ሰብሮ ማለፍ የሚያስችል አቅም አሳይቷል፡፡

በሰላማዊ ትግላችን ማለፍ የሚጠበቅብንን እርከን እየቆጠርን እያለፍን ነው፡፡ ያለፉት ሂደቶች አንድ፣ ሁለት፣ ሶስት፣ እየተባሉ የሚታለፉ የትግል ሂደቶች ነበሩ፡፡ መጪዎቹ ሂደቶች ግን ተቆጥረው የሚያልፉ ሳይሆን በዚያው ላይ ፅኑ በመሆን ድልን ሳይጨብጡ የማይታለፍባቸው ጊዚያት ሊሆኑ እንደሚገባ አመላካች ነገሮች አሉ፡፡ የትናንቱ ጁሙዓ ደግሞ ለዚህ ትልቁን መሰረት የጣለ ነው፡፡ በትናንቱ ጁሙዓ ጠንካራ መልእክት የተላለፈላቸው ውስጣዊም ውጫዊም ሃይሎች ነበሩ፡፡ በዋናነትም በእፎይታ ጊዜ ውስጥ መሆናችንን ተገን በማድረግ መንግስት እና የመንግስትን ፀረ አንድነት ፖሊሲ የሚያራምዱ አካላት ሜዳውን እንዳሻቸው ሲጠቀሙበት ቆይተዋል፡፡ ይህ ሁሉ ግን ህዝበ ሙስሊሙን ያስተሳሰረውን የአንድነት እና የፅናት ገመድ ሊፈታው አልቻለም፡፡ የትናንቱ ጁሙዓ የዚህ ትልቅ ማሳያ ነው፡፡ ሰላማዊ ትግላችን በማይዋዥቅ ፅናት እና በማይበጠስ አንድነት ላይ እንደተገነባ እስከድል በር ይደርሳል፤ ኢንሻአላህ!!!

ለትግሉ ፅናታችንን፣ ለወኪሎቻችንን ታማኝነታችንን ሁሌም እናረጋግጣለን!

ድምጻችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

Like ☑ Comment ☑ Share ☑

ይሄን ሊንክ ጠቅ አድርገው ይከተሉና አዲሱን የፌስቡክ ገጻችንን ላይክ ያድርጉ!
https://www.facebook.com/DimtsachinYisema2

ይህኛውን ሊንክ ጠቅ በማድረግ ደግሞ መደበኛውን ድረ ገጻችንን መጎብኘት ይችላሉ!
http://www.dimtsachinyisema.info/

ኢትዮጵያ ምሳሌ ልትሆንበት የምትችልበት ነገር ሃይማኖት ብቻ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ከሰማንያ በላይ ብሔር ብሔረሰቦችን በውስጧ አቅፋ የያዘች አገር ናት፡፡ አይደለም ሰማንያ ቀርቶ ሁለት ብሔረሰቦች ያሉባቸው አገሮች ግጭት ውስጥ ሲገቡ እናያለን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ጥቃቅን ግጭቶች የሉም ማለት ባንችልም፣ በአጠቃላይ ግን ለመኖር የሚያዳግት ግጭት ግን አስተናግዳ አታውቅም፡፡ ይህ ታሪካችን የሚያኮራን ቢሆንም፣ አሁን አሁን ግን የሚስተዋሉት ነገሮች ሃይ ሊባሉ የሚገባቸው ናቸው፡፡ ስለአብሮ መኖር ታሪካችን የማንጠነቀቅለት ከሆነ ይህ አኩሪ ታሪክ ሊበላሽና ሊጠፋ ይችላል፡፡ በተለያዩ ወቅቶች በአገሪቱ ውስጥ በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚነሱ የብሔር ግጭቶች የጉዳዩን አሳሳቢነት ሊያሳዩን ይችላሉ፡፡ በተለይም አገሪቱ ተስፋ የምታደርግባቸው እነዚህ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ጠባብ በሆነ የብሔር ፖለቲካ ውስጥ ገብተው ሲጋጩና ሲበጣበጡ ማየት አሳፋሪ ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአማራ ብቻ አይደለችም፤ ኢትዮጵያ የኦሮሞ ብቻም አይደለችም፤ ኢትዮጵያ የደቡብ ብቻም አይደለችም፤ ኢትዮጵያ የትግራይ ብቻም አይደለችም፤ ኢትዮጵያ የሁሉም ናት፡፡ ስለዚህ አንዱ ብሔር ከአንዱ ብሔር አይበልጥም፡፡ አንዱ ብሔር ከአንዱ ብሔርም አያንስም፡፡ ሁሉም እኩል ነው፡፡ አንዱ ከአንዱ ይሻላል በሚል ጽንፈኛ የብሔር ፖለቲካ አንድነታችንን ማፍረስ አይገባንም፡፡ የሁሉም ብሔሮች መገኛ የሆነችውን ኢትዮጵያን መመልከት ይገባል፡፡ በዚህም ረገድ ራሳችንን መሳል ተገቢ ነው፡፡ ያለበለዚያ ግን በየጊዜው እየዶለዶምን ሄደን አንድነታችንን ልናጣው እንችላለን፡፡ ሃይማኖቶች በመርህ ደረጃ አይጋጩም፡፡ ሁሉም ፍቅርን፣ መተሳሰብንና ሰላምን የሚሰብኩ ናቸው፡፡ ስለዚህ ሁሉም የመረጠውን ሃይማኖት የመከተል መብት አለው፡፡ ነገር ግን የአንድ ሃይማኖት ጠበቃ ነኝ በሚል የሌላ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ ምንም ዓይነት ተፅዕኖ ማድረግ ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ነው፡፡ ሰዎች በሚከተሉት ሃይማኖትና በማንነታቸው ፈጽሞ ሊፈረጁ አይገባም፡፡ ምክንያቱም ከሁሉም በላይ ሰውነታቸው ይበልጣልና፡፡ ስለዚህ ሰዎች ሐሳባቸውን በማንፀባረቃቸው ምክንያት በጠላትነት ሊፈረጁ አይገባም፡፡ ምክንያቱም ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ሕገ መንግሥታዊ ብቻ ሳይሆን ተፈጥሯዊም ነውና፡፡ ጽንፈኛ የሆነ አመለካከት በመያዝ የእኔ መንገድ ብቻ ነው ትክክል ማለት በ21ኛው ክፍለ ዘመን ኋላቀር የሆነ ብቻ ሳይሆን የማያስኬድ ነው፡፡ ስለዚህ ራስን በአንድ ሳጥን ውስጥ ጨምሮ እኔ ብቻ ያልኩት ይሁን ማለት አንድነታችንን ሸርሽሮ በኋላ ባዶ ሊያስቀረን ይችላል፡፡ በመሆኑም በሃይማኖቱም ሆነ በፖለቲካው እንዲሁም በሌላውም ጉዳይ የእኔ ሐሳብ ብቻ ይንገሥ ማለት ማንንም የትም አያደርስም፡፡ ስለዚህ በየትኛውም ጉዳይ ላይ ጽንፈኝነትን በማስወገድ አንድነታችንን ሊያጠናክሩ የሚችሉ ጉዳዮች ላይ ብናተኩር ሁላችንንም ይጠቅመናል ፡፡ ‪#‎ምንሊክሳልሳዊ‬

The road to democracy is a process not an event, and will require an ongoing struggle.
“Good governance is impossible without some sense of community,” Pro. Falk
Richard Falk

Amid the political turmoil spoiling the Middle East politics is a conceptual confusion that contributes to acute political alienation of those societal elements that feel subject to a governmental leadership and policy agenda that is perceived as hostile to their interests and values. Such circumstances are aggravated by political cultures that have been accustomed to “one-man shows” that accentuate tendencies towards adoration and demonisation.

Each national situation reflects the particularities of history, culture, values, and a host of other considerations, and at the same time, there are certain shared tendencies that reflect commonalities of experience, as well as the deformed import of Western hegemonic ideas of modernity, constitutionalism, and governance.

The recent political turmoil in Turkey and Egypt, each in its own way, is illustrative.

Same but different

In Egypt, this circumstance led to determined opposition to the elected leadership, especially to Mohamed Morsi, the president drawn from the ranks of the Muslim Brotherhood (MB). The aim of this opposition seemed to be to create a crisis of governability of sufficient depth to provoke a crisis of legitimacy, which could then produce a populist challenge from below that would bring together ideological demands for a different kind of political leadership and material demands for a better life. In the end, those who had pleaded so persuasively for freedom in Tahrir Square were two years later calling on the armed forces to engage in the most brutal expressions of counter-revolutionary vengeance.

In Turkey, such a collision has recently produced turmoil and highlighted the dangers and passions that accompany lethal polarisation, initially, in the encounters at Gezi Park and later, in a titanic struggle between Prime Minister Recep Tayyip Erdogan and Islamic leader Fethullah Gulen.

Turkey is different than Egypt in at least two major respects. First of all, its economy has flourished in the past decade, producing a rising middle class, and a business community with lots to lose if investor confidence and currency exchange rates decline sharply. This reality is complicated by the fact that part of those that have gained economically have been aligned with the AKP, and by the degree to which the Turkish armed forces are also major stakeholders in the private sector. Secondly, a major achievement of the AKP leadership has been to depoliticise the role of the Turkish military, partly to protect itself against interference and partly to satisfy European Union accession criteria.

Absence of community

Alienation and emotional distress is more a symptom than an explanation of why there exist such strong political tensions. Better understood, these conflicts are about class, religion, status, political style, and the benefits of governmental control. An additional source of public antagonism is the unresolved, and mostly unacknowledged, debate about the true nature of democracy as the ideal for good governance. One perplexing element is language, especially its use by politicians concerned with public opinion.

There is this impulse on one side to base governmental legitimacy on pleasing the citizenry, and on the other side, to insist upon fidelity to law and constitutionalism. Each side is motivated by unshakeable convictions, and has no disposition to listen, much less appreciate, what the others are saying. In effect, good governance is impossible without some sense of community, and what has become evident is that society unity is currently unattainable in the presence of the sort of alienation that has gripped the publics in Egypt and Turkey, and elsewhere.

Pining for old times

Part of the controversy can be reduced to these differences over the very nature of democracy, which needs to be qualified in one of two ways: majoritarian or republican. And here is the central tension: the public myth in all countries that deem themselves “modern” endorse the republican tradition of limited government and internal checks and balances, while the political culture is decidedly ambivalent. It can spontaneously legitimise the majoritarian prerogatives of a popular leader with strong societal backing. Those displaced, lament authoritarian tendencies that never troubled them in the past when they held the reins of governmental authority.

Part of the recent confusion is that sometimes the authoritarian tendency gets so corrupted that it loses support among those who share its class and ideological outlook, and a reformist enthusiasm emerges. This happened in Egypt, but its tenure was short lived as its adherents, drawn from the ranks of the urban educated elites, quickly realised that their interests and values were more jeopardised by the “new” order than it had been by the excesses of the “old” order.

The situation in Turkey is more subtle, yet exhibits several analogous features. Despite the outcome of elections that brought the AKP to power initially in 2002, subsequently reinforced by stronger electoral mandates in 2007 and 2012, most of the opposition never accepted these results as legitimate. In the background of this alienation was the implicit and feared belief that the AKP was mounting a challenge to the strong secularist legacy of Kemal Ataturk. With political acumen, the AKP manoeuvred pragmatically, creating a rapidly growing economy, proclaiming its fidelity to the secular creed, and by stages subjecting the armed forces to civilian control. Despite the magnitude of these achievements the AKP and Erdogan never gained respect from the anti-religious opposition. Strangely, this alienated opposition was never able to present a responsible opposition platform that could give the Turkish people a positive alternative.
Inside Story – Turkey: Political power struggle?

The Ataturk legacy included an acceptance of procedural democracy in the form of free and fair elections with the apparent implied assumption that the outcome would be faithful to his modernist orientation. When the AKP disappointed these expectations in 2002, the opposition became quickly fed up with the workings of “democracy”. Erdogan’s harsh style of discourse is particularly irritating to an already alienated opposition, reinforcing their belief that any alternative is better for Turkey than the AKP.

Similarly, the still obscure public falling out between the AKP and the hizmet movement has injected a new virus into the Turkish body politic. Perhaps Turkey is experiencing some of the mishaps associated with keeping a political party in power for too long. Such prolonged control of government almost inevitably produces scandal and corruption, especially in a political culture where the rule of law and the ethics of civic virtue have never been very strong.

Majoritarian or republican?

With this mix of considerations in mind, the distinction between “Majoritarian Democracy” and “Republican Democracy” seems important. In majoritarian democracy the leadership is essentially responsible to the electorate, and if its policies reflect the will of the majority, the views and values of opposed minorities need not be respected. Critical views treat such forms of government as susceptible to the “tyranny of the majority”. Arguably after Morsi’s election in 2012, and given the embittered opposition that seemed unwilling to accept the outcome of the vote, the MB used the prerogatives of office in a failed attempt to impose the majoritarian will.

“Republican Democracy” in contrast, starts with a generally sceptical view of human nature, and seeks above all to find procedures and support the nurturing of a political culture that prizes moderate government over efficiency and transcendent leadership. The American adoption of republican democracy is a classic instance of moulding a constitutional system that was wary of majorities and protective of minorities and of individual rights (although initially totally blind to the human claims of slaves and native Americans).

Delinking government from religious claims of certainty was also consistent with republican sensitivity to human flaws and the general ethos of Lord Acton’s famous saying “power corrupts, and absolute power corrupts absolutely”. Because over time every political system faces crises, the American founders realised that the envisioned arrangements would only survive the tests of time if two conditions were met: first, reverence for the constitution by both lawmakers and citizens, and second, judicial supremacy to override legislative and executive swings towards either implementing the momentary passions of the mob or aggrandising power and authority, and thereby upsetting the delicate balance of institutions.

It need hardly be argued that neither Egypt nor Turkey are remotely similar to the United States but the superficial embrace of democracy by these and other countries might benefit from examining more closely the menace of majoritarian democracy in a fragmented polity and the difficulties of establishing republican democracy in political cultures that have been so long controlled by militarism and authoritarianism.

Egypt is experiencing the essentially anti-democratic restoration of authoritarian militarism, while Turkey is trying to preserve sufficient stability and consensus to enable the self-restrained persistence of procedural democracy and a successful process of constitutional renewal that rids the country of the 1982 militarist vision of governance, and moves towards creating the institutional and procedural frame and safeguards associated with republican democracy. Such a vision of a democratic future for Turkey implies a process, not an event, and will require an on-going struggle inevitably distracted by crises of legitimacy. The hope is that calm minds will prevail; serving the long-term interests of a state that retains great potential to be a beacon of light in the region and beyond.

Richard Falk is Albert G Milbank Professor Emeritus of International Law at Princeton University and Visiting Distinguished Professor in Global and International Studies at the University of California, Santa Barbara. He is also the United Nations Special Rapporteur on Palestinian human rights.

The views expressed in this article are the author’s own and do not necessarily reflect Al Jazeera’s editorial policy.
Richard Falk is Albert G Milbank Professor Emeritus of International Law at Princeton University and Visiting Distinguished Professor in Global and International Studies at the University of California, Santa Barbara. He is also the United Nations Special Rapporteur on Palestinian human rights.
http://www.aljazeera.com/indepth/opinio … 17430.html

AFRICANGLOBE – After all attempts to solve the Egyptian-Ethiopian crisis over the Renaissance Dam at the negotiating table ended in failure after a third round of negotiations on Jan. 4, with Egypt withdrawing from the discussions and conferences being held in Khartoum, there is now talk at the governmental level about internationalizing the issue. At the same time, Egypt is witnessing rising popular demands to resort to the UN Security Council to establish Egypt’s right to veto the establishment of the Renaissance Dam, given the potential danger it represents to Egyptian water security.
Image
Khalid Wasif, the official spokesman for the minister of irrigation and water resources, revealed to Al-Monitor that Egypt has “begun to explore international channels for setting up alternative diplomatic and political tracks to ward off the dangers that might afflict the country if the Renaissance Dam is built, in light of the announced specifications of the dam.” He emphasized, “Egypt will not allow the dam to be built and will move to rally international pressure to prevent it from being funded. Moreover, Cairo will work [to secure] a public declaration by the international community rejecting the dam’s completion, in the absence of [Ethiopian] guarantees that Egypt and Egyptians will not suffer any loss in water security, nor will the other states of the Nile Basin. Egypt has rights guaranteed by international law and agreements, which the Ethiopian side is not respecting.”

Wasif added, “According to existing agreements governing the river — which require upriver states to notify Egypt in advance and obtain its consent prior to embarking on any projects that would affect the Nile sources — Egypt’s is the stronger legal position. Yet, Egypt has nevertheless insisted upon resolving the issue in a friendly manner, through reciprocal dialogue with the Ethiopian side, devoid of any escalation. But the government in Addis Ababa has shown no appreciation for this fact. Thus, Egypt has refused to continue the latest Khartoum meetings, given Ethiopia’s insistence on not providing the necessary guarantees that Egypt’s share of the water supply will remain secure.”

Rida al-Dimak, the director of the Center for Water Projects at Cairo University’s Engineering College, told Al-Monitor, “The development of alternative supplies of water must be accelerated, to replace the water that will be lost as a result of the construction of the Renaissance Dam. Foremost among these alternative sources is the exchange of wellspring [water] with the [Democratic Republic of the] Congo, transferring water from the Congo River to the Nile, so as to guarantee that the amount of water available to Egypt remains constant.”

Dimak warned against the completion of the Renaissance Dam according to its current specifications, stating that it would constitute a violation of human rights. The social and environmental effects, he explained, must be taken into consideration whenever a new water project is built, in accordance with inviolable international conventions. Some international reports have confirmed that the Ethiopian dam will result in a shortage of drinking water and destruction of a great deal of Egyptian agricultural land. This, he states, provides the foundation for Egypt’s right to object to the dam in international forums.

For his part, former Minister of Irrigation and Water Resources Muhammad Nasr al-Din Allam said in an interview with Al-Monitor that the Egyptian government no longer has any alternative but to move quickly to take steps toward international escalation. The first of these, he states, should be to lodge an official protest against the government in Addis Ababa, formally declaring Egypt’s rejection of the project.

“This right is guaranteed to us by old agreements signed and recognized internationally, and which were conditioned upon notifying Egypt in advance before any Nile-related project was established. This protest ought to be followed by the lodging of an official complaint with the UN to establish Egypt’s position and [remonstrate against] Ethiopian intransigence, as well as to formally demand the formation of an international fact-finding committee to study the points of disagreement between Egypt and Ethiopia. These points include the dam’s capacity, the period of time needed to fill it, [details concerning its] operation, the project’s unsound and unsafe construction and the lack of rigorous Ethiopian studies demonstrating that the dam is not vulnerable to collapse, something that would have disastrous consequences for both Egypt and Sudan,” Allam noted.

Allam stressed the need for Egypt to demand that construction on the Ethiopian dam be halted at once, until the fact-finding committee completes its work. According to Allam, this would require “a period of, at most, three to six months.” Moreover, he added, “A copy of the committee’s report should be brought before the UN, to demonstrate the damage that the dam would wreak upon Egypt, which should then head to the Security Council.”

In an interview with the daily El Fagr on Jan. 9, Ayman Salama, an Egyptian expert in international law, stressed that the Egyptian government would be justified in taking its case to the UN Security Council, even though “one cannot adopt international arbitration to settle the crisis, since that would require the assent of both parties to the conflict to adopt this formulation of crisis resolution. The Ethiopian government has indicated that it will be highly intransigent on this issue. International arbitration has therefore become extremely unlikely. But Egypt might be able to turn to the Security Council. This, however, would require the preparation of a file containing documented facts of legal and material evidence of the harm that this dam would incur, both to Egypt and to its vital interests. The issue must be shown to threaten the peace and security of the two countries. [If successful], a number of measures could then be taken by the Security Council to compel Ethiopia to meet Egyptian demands.”

Egypt’s National Defense Council has already held an emergency session on Jan. 8, headed by President Adly Mansour and dedicated to reviewing internal developments and the domestic Egyptian security situation. With the irrigation and water resources minister in attendance, the council also examined the latest developments concerning Ethiopia’s Renaissance Dam and the steps being taken on that front to preserve Egyptian water security. It also noted the steps devoted to reducing or eliminating any negative effects that the soon-to-be-built dam might have on Egypt or the other states of the Nile Basin. The council also stressed that Egypt’s water rights must not be squandered, and that it would not accept any undermining of Egyptian national security.

These steps, and Egyptian moves toward international escalation and the internationalization of the Renaissance Dam crisis, follow years of Egyptian insistence upon solving the crisis through mutual dialogue at the negotiating table.

By: Walaa Hussein
http://www.youtube.com/watch?feature=pl … _mpjU2qIdc

http://www.africanglobe.net/africa/egyp … m-project/

Image
Kilef Kassa (left) and Micheal Aynkulu struggled to keep their candles lit at Thursday’s vigil. About 200 people attended the event at the 7-Eleven where Yosef Tulu worked.

GARLAND — Sobbing punctuated prayers and song during a candlelight vigil Thursday night to remember the 7-Eleven clerk whose promising life was abruptly ended in a shooting this week.

Friends, family and many who barely knew Yosef Tulu came out to the Garland store where he was slain to mourn the Ethiopian man, who had moved to America with dreams of a better life for himself and his fiancée.

The gathering culminated a day in which police announced that Colten Jon Moore, the Garland teen accused of killing 31-year-old Tulu early Tuesday, had also confessed to a shooting reported Jan. 16.

The victim in the earlier shooting, who also was shot at a convenience store while on duty as a clerk, survived the attack, said Garland police spokesman Joe Harn.

“Had we not found him for the murder, we would still not know who did that shooting a week ago,” Harn said of Moore, 18. “Nobody saw him. There was no video of him.”

Tulu was shot after handing over money and cigarettes to a masked man with a scoped rifle early Tuesday. The gunman then forced him to lie down behind the counter and shot him twice, police said. A spent .22-caliber Remington casing was found near Tulu’s body.

Friends of Moore’s came forward after police released surveillance video from the shooting. The friends told police that they had seen Moore wear a hunting mask similar to one seen in the video, according to an arrest warrant affidavit released Thursday.

Moore had been telling friends for more than a year that he wanted to shoot someone with his father’s rifle and make it look like a robbery, the affidavit says. The friends told police that he had said he planned to take the gun from its locked case while his father slept and return it later, the document says.

Police had received no tips about the teen before the shooting, Harn said.

Moore was in the Dallas County Jail on Thursday, charged with capital murder in Tulu’s death and aggravated assault in the other shooting. Bail was set at $1 million on the murder count. The bail amount had not been announced on the other charge.

On Jan. 16, police responded around 11:40 p.m. to the Homeboy’s gas station in the 2500 block of Firewheel Parkway, across the street from the 7-Eleven where Tulu was shot. A clerk had stepped outside the station and was shot twice before he got back inside to call for help, police said.

The clerk was probably shot with the same rifle used to kill Tulu, Harn said. The victim, who has not been identified, remained hospitalized at Medical Center of Plano and was expected to be released Friday, Harn said.

The Dallas County Jail website listed Moore’s lawyer as Brad Lollar, who did not respond to a request for comment Thursday night.

Attempts to reach Moore’s immediate family members were unsuccessful. Reached by phone, Moore’s godmother, who did not want her name used, said the family would have no comment.

Some parents whose children attended high school with Moore said their kids thought of him as a nice, “cool guy,” not anybody who stood out.

One of Moore’s teachers at Richland College said the teen was social but arrogant in class. Moore was studying graphic design at the school, according to his Facebook page.

The teacher, who asked not to be named, said Moore was confrontational with his teachers but didn’t seem dangerous.

Moore was arrested in December in Garland for public intoxication. He was arrested in May on a charge of marijuana possession in Brown County; he received probation.

Despite the cold weather, about 200 people attended Thursday’s vigil, including a large turnout of Ethiopians. A small mountain of flowers and stuffed animals piled up near the entrance to the 7-Eleven.

Andualem Shoro, Tulu’s brother-in-law, made a brief statement thanking Garland police and asked for prayers for both families.

Martha Tamrat and Ameha Gebremichael said they didn’t know Tulu but wanted to show support.

“It’s really painful for everybody,” Gebremichael said. “Everyone is coming here to make money, support family back home, and a lot of family may depend on this guy.”

Tulu moved to Garland from Ethiopia about five years ago, leaving behind his fiancée, said Bayelegn Megeren, a friend of Tulu’s sister-in-law.

“He had a lot of plans,” Megeren said. “They’re cut short.”

Megeren described Tulu as hardworking. He was enrolled in school to become a nurse and planned to return to Ethiopia in the next few months to marry his fiancée and bring her back to Texas, he said.

“When I saw his picture, Yosef could have been my son,” said Mac Mekonnen, a leader of North Texas Ethiopians. “Yosef came to this country like all of us; we migrated for better opportunity, to catch that American dream.”

Only a handful of vigil attendees knew Tulu, but his smile and kindhearted demeanor touched many, including Sarah Ryan.

Ryan, who used to work at the Tom Thumb next to the 7-Eleven, said Tulu was always friendly and “had a smile for everyone.”

“It’s one of those instances where bad things happen to the very best people. It’s not fair.”

[email protected];

[email protected]

HOW TO HELP: Fund for Tulu’s kin

7-Eleven Inc. has set up a fund at Chase Bank to help Yosef Tulu’s family through donations. The account number is 555289953.

7-Eleven also announced this week that it would help Tulu’s family with expenses related to transporting his body back to Ethiopia. The company also has offered professional counseling services to store employees.

From staff reports

Image

Ethiopia’s opposition politician Bekele Gerba is not legible for release until next month and may not be released until next year, Horn Affairs learnt.
Bekele Gerba, former dep. Chairperson of Oromo Federalist Democratic Movement (OFDM), was detained in August 27, 2011. He was sentenced to eight years imprisonment on charges of “provocation crimes against the state” and collaborating with the Oromo Liberation Front, an organization designated as terrorist by Ethiopian Parliament.
The sentence was reduced to three years and seven months after Bekele appealed to the Federal Supreme Court.
There have been claims on social media that Bekele was supposed to be released on probation last weekend, but has been kept in prison for bureaucratic reasons.
Public Relations officer of the Federal Prison Administration Commission contradicted the claims.
Addisu Tedros told Horn Affairs today that:

“A prisoner’s release on probation is determined based on a thorough evaluation and finally submitted to court for approval. However, Bekele Gerba’s case has not reached that stage yet.
If Bekele Gerba is to be released on probation it would not be sooner than February 10, 2014. Otherwise, his prison term will end on May 11, 2015.”

Asked whether the dates are counted correctly, the officer added that it is based on a computerized data base.
On the other hand, a senior official in the Ethiopian government told Horn Affairs that Bekele Gerba won’t be released on probation.
The official, speaking off-the-record, said that: “The government has no intention of releasing [Bekele Gerba] until he completes the full prison term.”
No more pre-release of prisoners?
The Ethiopian government has not released any high-profile prisoner since the pardon for the two Swedish journalists on September 2012, when Prime Minister Hailemariam Desalegn was still an acting PM. Though tens of thousands have been granted pardon on the eve of the Ethiopian New Year, last September, there are reports that the government rejected the petition for pardon by journalist Wubshet Taye and opposition politician Zerihun G/Egiziabher.
Remarking on the matter, during an exclusive interview with Horn Affairs last week, Minister Rewan Husien claimed that this doesn’t mean that the government has closed the door on pre-release of prisoners.
Referring to the high-profile prisoners, Redwan added:
“Currently, the government has not arrived at a conclusion that there is anyone who is ready to change, who has been corrected and who has reached a point of becoming an example to others. But that doesn’t mean we won’t reach a different conclusion at some future date.”
Though Redwan was commenting on pardon – which is technically different from a release on probation -, both matters lie under the discretion of the government. Thus, presumably subject to similar raison d’etre.

After World War II, Ethiopia began to receive economic development aid from the more affluent Western countries. Originally the United Kingdom was the primary source of this aid, but they withdrew in 1952, to be replaced by the United States. Between 1950 and 1970, one source estimated that Ethiopia received almost US$600 million in aid, $211.9 million from the US, $100 million from the Soviet Union and $121 million from the World Bank. Sweden trained the Imperial Bodyguard and India at one point contributed the majority of foreign-born schoolteachers in the Ethiopian educational system.
This aid dried up under the military regime that followed the Ethiopian revolution, except for food aid during the mid-1980s. While the Soviet Union provided extensive amounts of aid, either directly or through its allies like East Germany and North Yemen, this was predominantly in the form of either military aid, or ideological education; these ended with the close of the Cold War. Large aid inflows resumed in the early 1990s aimed at reconstruction and political stabilization but declined during the war with Eritrea. The post-2000 period,however, has seen a resumption of large disbursements of grants and loans from the United States, the European Union, individual European nations, Japan, the People’s Republic of China, the World Bank, and the African Development Bank. These funds totaled US$1.6 billion in 2001.
In 2001 Ethiopia qualified for the World Bank-International Monetary Fund-sponsored Highly Indebted Poor Countries (HIPC) debt reduction program, which is designed to reduce or eliminate repayment of bilateral loans from wealthy countries and international lenders such as the World Bank.
A noteworthy advance toward these goals came in 1999, when the successor states to the former Soviet Union, including Russia, cancelled US$5 billion in debt contracted by the Derg, a step that cut Ethiopia’s external debt in half. HIPC relief is expected to total almost US$2 billion.

TPLF took the country without loan . Russia cancelled US$5 billion in debt contracted by the Derg .. after that the TPLF junta have got over 50 billion Dollars loan in the name of Dev`t but most of the money spent for corruption and to rebuild TIgray . There is no balanced development in Ethiopia.

የሱዳኑ ፕሬዚደንት ኦማር ሀሰን አልበሺር በኤርትራ ያደረጉት ጉብኝት የሁለቱን ኣጎራባች ኣገሮች ግንኙነት ከማጎልበት ጎንለጎን በአካባቢያዊ እና ዓለም ዓቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መሆኑ ተገለጸ። ኣልበሺር ከኤርትራው አቻቸው ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ባደረጉት የሶስት ቀናት ቆይታ የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታን ጨምሮ በተለይም የኢትዮ ኤርትራን የሰላም ንግግር ስመልክቶ መነጋገራቸውን ምንጮች ኣመልክቷል።
የኣሁኑ ውይይት በሁለቱ ተደራዳሪ ኣገሮች በኩል ሊቀርቡ በሚችሉ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ነበርም ተብሏል።

የሱዳኑ መሪ ኦመር ሓሰን ኣልበሺር፣ ባለፈው ሳምንት በኤርትራ ያደረጉት የሶስት ቀናት ጉብኝት፤ የሱዳኑ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ኬርቲ ለዜና ወኪሎች እንዳስረዱት፤ የሁለቱን ኣጎራባች ኣገሮች ግንኙነት በማጎልበት ላይ ያተኮረ ነበር። የኣልበሺር ጉብኝት ባለፈው ህዳር ወር የኤርትራው ኢሳያስ አፈወርቂ በሱዳን ያደረጉትን ጉብኝት ተከትሎ የተደረገ መሆኑን የጠቀሱት የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ኬርቲ በዚህ ግንኙነት ሁለቱ መሪዎች ከዚህ ቀደም የተፈረሙ የውል ስምምነቶች ሊተገበሩ ስለሚችሉባቸው ዝርዝር ጉዳዮች ላይ መምከራቸውንም ኣስረድቷል።
ባለፈው ማክሰኞ ኤርትራ ሲገቡ ደማቅ ኣቀባበል የተደረገላቸው ኣልበሺር ከኣስመራ ውጪ ያሉ ኣንዳንድ ከተሞችንም የጎበኙ ሲሆን በኤርትራ 21ኛ ዓመት የነጻነት በዓል ላይም ተገኝተው ነበር። ሁለቱ መሪዎች፣ ኣልበሺር እና ኢሳያስ፣ የዔርትራው ገዢ ፓርቲ የፖለቲካ ጉዳዮች የበላይ፣ የማነ ገ/ዓብ፣ ለዜና ምንጮች እንደገለጹት፣ የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታን ጨምሮ በበርካታ አካባቢያዊ እና ዓለም ዓቀፋዊ ጉዳዮች ላይ የመከሩ ሲሆን ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ደግሞ ኣንዱና ዋናው የመሪዎቹ አጀንዳ የኢትዮ ኤርትራ የሰላም ንግግር ነው ተብሏል።
በኖርዌይ ኣገር፣ ስታቫንገር ዩኑቨርሲቲ፣ የፖለቲካል ሳይንስ እና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር ግሩም ዘለቀ እንደሚሉትም የኣልበሺር የኣስመራ ጉብኝት የሰላም ንግግሩ የመጀመሪያው ምዕራፍ ሲሆን በሁለቱ ወገኖች በኩል ሊቀርቡ በሚችሉ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል።
እርቀ ሰላም መውረዱ ለሁለቱም ኣገሮች በተለይ ም ደግሞ ዶ/ር ግሩም እንደሚሉት ለኤርትራ ከፍተኛ ጠቀሜታ ነው ያለው።
ከኤርትራ በኩል በጉዳዩ ላይ እስከ ኣሁን ይፋ የሆነ መግለጫ ባይኖርም በኢትዮጵያ በኩል ግን፤ የጠ/ሚኒስትሩ ቃ/አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ እንደሚሉት፣ ቀደም ሲል የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች እንደተጠበቁ ሆነው ለመደራደር ግን መንግስት ዝግጁ ነው።
በዚህ የሰላም ንግግር፤ ከተሳካ ማለት ነው፤ ተጠቃሚዎቹ በዋናነት ሁለቱ ኣገሮች ቢሆኑም ዶ/ር ግሩም ዘለቀ እንደሚሉት ደግሞ ኣልበሺርም ቢሆኑ በግልም ጭምር ተጠቃሚ መሆናቸው መዘንጋት የለበትም።
ከተገንጣዩዋ የደቡብ ሱዳን መንግስት ጋር ካለባቸው የግዛት ይገባኛል ውዝግብ በተጨማሪም የዳርፉር ቀውስን ጨምሮ በሰሜን ኩርዱፋን እና በብሉ ናይል ግዛቶችም በውስጥ ችግሮች ተጠምደው የሚገኙት ኣልበሺር ምንም እንኳን ከኣፍሪካ ህብረት በኩል አንጻራዊ ተቀባይነት ቢኖራቸውም በምዕራባውያኑ ዘንድ እንደ ወንጀለኛ መፈረጃቸው ይታወቃል። በዚሁ የተነሳም ዓለም ዓቀፉ ፍ/ቤት ICC የእስር ማዘዣ እንደቆረጠባቸው ይገኛሉ።

ማንኛውም አንድን ሃገር እመራልሁ የሚል …የበላይ መመሪያ እና ህዝብን የሚያስተዳድርበት ህገመንግስት አለው:; የወያኔ ጁንታም በራሱ የፓርቲ ፕሮግራም መሰረት ተደርጎ አለማቀፍ ህጎች ተዋህደውት በራሱ ካድሬዎች ውክልና እና ስብስብ የጸደቀውን ህገመንግስት ለህገወጥ ተግባር እያዋለው ነው:: አንድ ህዝብ ህግን ሊያከብር የሚችለው ራሱ ወይንም ተወካዮቹ ባረቀቁለት ህግ እና ህገመንግስት መሆኑ እሙን ነው::ጨዋው ይሪትዮጵያ ህዝብ ግን እንደፈለጉ የሚያመጡለትን ህግ አንገቱን ሰብሮ በማክበር ሲኖር ገዢዎቹ ግን ራሳቸው ያወጡትን ህግ ሀገወጥ መሆኑን በአደባባይ ያስመሰከሩበት አጋጣሚዎች እጅግ ብዙ ናቸው::

በሃገሪቱ ህገመንግስታዊ መዋቅር እና መነባበብ የሌሉባቸውን ያለፍት ህገወጥ 22 አመታቶች በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የበላይነት የተዳደሩ ወይንም ያለፉ የሰው ልጆችን ይወክላሉ የሚባሉ ህጎችን ማግኘት አስቸጋሪ ነበር::ምንሊክ ሳልሳዊ በዘፈቀደ የበላይ የፓርቲ አመራሮች በሻቸው ሰአት ህጎችን በማውጣት እና በማጽደቅ ህዝብ ላይ እንደፈለጉ ይጨፍራሉ:: ህዝብ ለህገመንግስቱ ያለ ግንዛቤ አናሳ መሆኑን እና ማን እንዳወጣው እንዴት እንደወጣ ስለሚያውቁት ህዝቡ ያሌለበት ተሳትፎ እንደሆኑ ስለሚረዱት እንዳሻቸው ህገመንግስቱን ይጥሉታል ያነሱታል:: የወረቀት ላይ እይታ ብቻ አድርገው በማስቀረት ህገወጥነትን አስፋፍተዋል::

በወያኔ ውስጥ ተስፋፍቶ የሚገኘው መንግስታዊ ህገወጥነት ከእይታ ያልተሰወረ ሲሆን ህዝብ በህገመንግስቱ መሰረት ፍትህ ማግኘት ሲገባው ፍትህን አቶ እየተንደፋደፍ ይገኛል::ህዝብን በፍትህ እጦት የታረደ ዶሮ ያደረገው ወያኔ የፍትህ አከላት ከህገመንግስቱ ውጪ ህገወጥ የሆኑ ያልተጻፉ ህጎችን ሲጠቀሙ ያየ ወይንም ለምን ያለ መንግስት የለም::የፍትህ አከላቶች ህገን ለማስከበር እና ህግን ለመተርጎም የተቋቋሙ አካላት ሆነው ሳለ በፖለቲክ ትብትቦሽ ተይዘው ሕገ መንግሥቱን በሚያሽመደምድ ሕጎችን በሚጥስ መንገድ እነ ..እንዳይጠየቁ ወይም እንዳይከሰሱ፣ ከተከሰሱም እንዳይሸነፉ የሚንቀሳቀስና የሚሯሯጥ በፍትህ አከላት ውስጥ በድብቅና በሕገወጥ የተገነባ አካል በይፋ በትንንሽ መመሪያዎች እና ትእዛዞች ህገመንግስቱን ደፍጥጦታል::

ሌላው በወያኔ ጁንታ ውስጥ እየተደረገ ያለው ህገመንግስታዊ ህገወጥ ንቅዘት የዜጎች የመኖር ህልውና እና ሰርቶ የማደር ጉዳይ ሲሆን አለማቀፍ ድንጋጌዎችን የጣሰ እና ህገመንግስቱት የጣለ ከፍተኛ የሆነውን ህዝብ ለስደት ያበቃ የጸረ ህልውና እንቅስቃሴ በገሃይ እያየን ነው::ይህ ደሞ የወለደው የወያኔ ባለስልታናት በሚያደርጉት ህገወጥ የኢኮኖሚ ወረራ ምክንያት ህዝቦች በሃገራቸው እንዲሽመደመዱ ሲያደርግ ሰርቶ የመኖር ህልውናን ገደል ከቶታል::ባእስልጣናቱ ህዝቦች በፈለጉት የስራ መስክ እንዳይሰማሩ ሙስናን እና ንቅዘትን በስፋት በስራ ላይ አውለውታል::

እነዚህ የተፈጠሩ መንግስታዊ ህገወጥነቶች ሕዝብ መንግስት እንዳሌለ አምኖ እንዲቀበል አድርገውታል፡፡እኩልነት እንዳሌለ አረጋግጠዋል፣ ሕገ መንግሥቱም አለኝታዬ አይደለም እንዲል አድርገውታል፡፡ ምክንያቱም ሕግ አክብሩ ከሚባሉ ዜጎች ጎን ለጎን ከሕግ በላይ የሆኑና ተመልሰው መንግሥትን የሚጫኑ፣ የሚይዙና የሚያስፈራሩ ሌሎች ዜጎች እንዳሉ ሕዝብ በተግባር አይቷል፡፡ እነሱንማ ማን ይነካቸዋል እያለ መንግሥት ዜጎችን ከሕግ አንፃር በእኩልነት ያያል የሚለው እምነቱ ተሟጧል፡፡የተቃወሙትን መብታቸውን የጠየቁትን ሁሉ ልማቱን ያደናቅፋሉ፡፡በማለት… የወያኔ ባለስልጣናት ከአገርና ከሕዝብ በላይ ነን ብለው አገር ለእነሱ በምትስማማበትና በምትገዛበት መንገድ እንድትጓዝ ይፈልጋሉ እንጂ ከእነሱ ጥቅም፣ ክብርና ዝና ውጭ ህዝቦች በህግ ተዳደሩ አልተዳደሩ አጀንዳቸው አይደለም፡፡ለምን ቢባል ጥይት እንዲገዛቸው ይደረጋል:: እነዚህ ሕገወጥ የወያኔው ቡድኖች አገርን እየዘረፉ፣ የአገር ገንዘብ እያሽከረከሩና የሰው ልጆችን መብት እየጣሱባለበት ወቅት ህዝብ በቃኝ ብሎ ሕገወጥነትን ለማፈራረስ ሲረባረብ በጥይት ይቆላል ይወነጀላል::(ምንሊክ ሳልሳዊ)

ወያኔ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ ወደ ልማታዊ ዲሞክራሲ ተለውጫለሁ በማለት እያጭበረበረ ነው፡፡ ሕዝቡን ከድህነት ለማላቀቅ፣ ሙስናን ለመዋጋት የቆምኩና የቆረጥኩ ነኝ በማለት እያደናበረ ነው፡፡ የሕግ የበላይነት የሚለውን አባባልም በየዕለቱ ለሚዲያ ፍጆታ እየዋለ ነው፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን እና አደርባይነትን ማውገዝ ከዕለቱ የሜትሮሎጂ ሪፖርት በላይበተጋነነ መልኩ በተደጋጋሚ የምንሰማው ነው፡፡ በወያኔ መዋቅሮች ውስጥ ተሰግስገው ያሉት ሕገወጥ ንቅዘቶች ግን የማይፈርስ መሰረታቸውን ተክለው እየተንቀሳቀሱ ነው::ይህን ለነገ አደጋ እንዳለው ያልተረድው ወያኔ ራሱን ማዳን ወደማይችልበት አዘቅት ውስጥ እንደገባ እሙን ነው:; (ምንሊክ ሳልሳዊ)

After the government held an evaluation regarding the leakage of information, disarray in information keeping and cyber intelligence, members of the intelligence have asked to whom they were answerable to. ESAT obtained audio supported evidence regarding the query from sources in the Intel office. High government officials and appointees also attended the meeting.

The question was posed by Intel officers working under the Federal government and graduates of the Mekele Institute of Technology (MIT), an institute founded under the cover of MekeleUniversity during the period in office of the late Prime Minister Meles Zenawi.

“Is our responsibility protecting the security of the Nation or the political regime?” asked the officers. A senior government official responded saying “there is no Intel officer who also does not have political duties. From the outset, intelligence is a work of sustaining a regime in power and this is done by professionals. It requires one to trust the regime. One who believes in Ginbot 7 Movement’s outlook and thinks that the regime should be removed through force, would disintegrate the system even if he is remarked for having the skills of Tesfaye Woldeselassie or was trained by Mossad for 20 years.”

It was also discussed during the evaluation that there is a difference and fall out within the chain of commands of the Nationality and Immigration Department, Defense Intelligence, Ministry of Foreign Affairs, Federal Police, Anti-Terrorism Taskforce and Information Network Security Agency (INSA).

Some government officials have said that secrets of the government have been passed to third parties to the extent that it has become impossible to protect secrets.

Intel officials that came from Oromia and Southern regions complained why there was a dominance of one ethnic group within the Defense Intelligence. The official responded saying that balancing the Force was a long-term work.

Responding to the question that there is a rumour that Meles Zenawi was killed by foreign forces, the official said Meles died due to “huge workload and his inability to put up with the medical treatment”.

In the mean time, five members of the Ethiopian National Intelligence and Security Service have been detained suspected of working and passing information with and to Ethiopian Satellite Television (ESAT). Mebrate Tamrat, Jemal Awol, Dejene Admas, Hailu Cherkos, Capitan Assefa Abraha have been detained by securities.

Similarly, students and intelligence heads found in the 28 universities of the Country have started an evaluation meeting. It has been decided during the evaluation that Aksum, Debre Tabor and Debre Birhan Universities have witnessed huge protests thus should be under stringent Intel surveillance. ESAT News

An Ethiopian government official said the border demarcation controversy between Ethiopian and Sudan has no legal backing but moral and social questions. The official said this during an evaluation and meeting of Intel officers and high government officials.

The official said the demarcation process started in 1965 between the then Ethiopian Minister of Foreign Affairs, Dr. Minase Haile and his Sudanese counterpart Jaafar al-Nimeiri and has been lingering since.

He said based on the complaints received that the Sudanese have passed the Ethiopian border line of Guwi, a committee had been formed which has not yet conducted any form of border demarcation.

The official said on a recent high level meeting Sudanese officials came up with a new suggestion. The Sudanese said “you can still hold the land. We will protect the rights of your citizens. But at least in terms of principle, accept and confirm that the land belongs to us.”

The Ethiopian official told the officers that if one checks out his mobile apparatus near the borders of Ethiopia and Sudan such as Berehet in Tigray or Armachiho near Gonder it shows you that you are in the Sudan. So you may fake politics but not the science, he added.

He also said that recent reports that Armachiho has been given to Sudan is wrong but some Sudanese police officers do at times sneak in to the border towns of Ethiopia start havoc but our militias do not hold down rather they do not even consider the Sudanese soldiers as ‘soldiers’.

He said it does not mean that we can take hold of anything that our eyes see in fact if we want to do so we can even capture Khartoum.

The official asserted that the border demarcation has not at all started so far.

The online news source, Sudan Tribune, had reported quoting the region’s administrator in 2007 that a large chunk of land had been given to the Sudan.ESAT News

Eritrea is among the most closed countries in the world; human rights conditions remain dismal. Indefinite military service, torture, arbitrary detention, and severe restrictions on freedoms of expression, association, and religion provoke thousands of Eritreans to flee the country each month. Among those fleeing in 2013 were the minister of information—whose 85-year-old father, brother, and 15-year-old daughter were immediately arrested—and the deputy head of economic affairs of the People’s Front for Democracy and Justice (PFDJ), Eritrea’s sole political party that controls most major domestic commercial enterprises.

In October, more than 300 Eritrean refugees drowned when a boat bringing them to Europe capsized near Lampedusa, Italy. According to the United Nations High Commissioner for Refugees (UNHCR), over 305,000 Eritreans (more than 5 percent of the population) have fled during the past decade.

Eritrea has no constitution, functioning legislature, independent judiciary, elections, independent press, or nongovernmental organizations; it does not hold elections. All power is concentrated in the hands of President Isaias Afewerki, in office since 1991.

In a rare sign of domestic dissent, on January 21, 2013, a group of soldiers with tanks, led by a brigadier general and three colonels, briefly occupied the Ministry of Information (“Forto”) and forced the director of government television to read a statement demanding the release of political prisoners and implementation of the 1997 constitution. The transmission was cut after a few sentences and the protestors surrendered when other military units failed to deliver expected support. According to credible reports, 60 or more high-level alleged collaborators were arrested, several of whom are now dead, some by suicide. Among them is said to be Abdella Jaber, PFDJ’s chief administrator.

Despite repeated requests, Eritrea denied the United Nation special rapporteur on Eritrea, Sheila Keetharuth, a visa. In a 2013 report based on refugee interviews, she concluded that “basic tenets of the rule of law are not respected.” Following her report, the Council “strongly condemn[ed]” Eritrea’s “continued widespread and systematic violations of human rights and fundamental freedoms.”

Indefinite Conscription and Forced Labor
Eritrea conscripts all men and unmarried women into “national service.” Although Eritrean law limits national service to 18 months, most conscripts serve for much of their working lives. Conscripts are routinely used as forced labor on essentially civilian jobs. In 2013, Human Rights Watch reported that conscripts were used by a state-owned construction company, Segen Construction Co., engaged by Canadian mining firm Nevsun Resources, to build infrastructure at its Bisha gold mine. Former conscripts described working long hours for minimal food rations, primitive lodging, and wages too low to sustain themselves, much less their families. They were not allowed to leave the work site.

Children as young as 15 are inducted and sent for military training, according to recent interviews by refugee agencies. They and other recruits are regularly subject to violence and ill-treatment for raising questions or for other perceived infractions. Beatings, torture, and prolonged incarcerations are common. Women are subject to [deleted] violence from military commanders, including rape. No mechanisms for redress exist.

Since mid-2012, all men in their 50s, 60s, and 70s are compelled to perform militia duty: carrying military weapons; reporting for training; and going on periodic patrols.

Arbitrary Arrest, Prolonged Detention, and Inhumane Conditions
Thousands of ordinary citizens are arrested and incarcerated without charge, trial, or opportunity to appeal, and without access to family, lawyers, or independent prison monitoring organizations. While some are freed without explanation and warned not to speak about their detention, most prisoners remain in jail indefinitely. Until the “Forto” incident in January 2013, the most prominent prisoners were 21 government officials and journalists arrested in September 2001 and still held incommunicado 12 years later. None have been formally charged, much less tried; former guards who have left Eritrea report that half of them have died.

Former detainees describe brutal detention conditions. Death in captivity is not unusual. Many prisoners disappear, their whereabouts and health unknown to their families. Former prisoners describe being confined in vastly overcrowded underground cells or shipping containers, with no space to lie down, little or no light, oppressive heat or cold, and vermin. Medical treatment is poor or non-existent. Food consists of a piece or two of bread a day, occasional servings of lentils or beans, a cup of tea, and insufficient water. Beatings and torture in detention are common; wardens are able to impose any physical punishment they devise. A former interrogator told Human Rights Watch he ordered beatings of prisoners until they confessed to whatever they were accused of; they were then beaten to implicate others.

Eritreans who were forcibly repatriated to Eritrea from Middle Eastern countries and then fled again told Human Rights Watch in 2012 they had been incarcerated in crammed cells and beaten shortly after their return. They displayed scars from beatings and electric shocks. One escapee reported that several prisoners in his group of returnees died from their beatings.

Freedom of Religion
Since 2002, the government has jailed and physically abused citizens for practicing religions other than the four government-controlled or recognized religions—Sunni Islam, Ethiopian Orthodox, Catholicism, and Lutheranism. Most arrests occur in private houses but many also occur during private Quran or Bible study at colleges or at national service training centers.

Some prisoners are offered release on condition that they sign statements renouncing their faith. Three deaths during captivity were reported by foreign-based religious monitoring groups in 2013, but given the difficulties of obtaining information, the number may be higher.

The octogenarian Orthodox patriarch, whom the government deposed in 2007, remains under strict house arrest.

Reprisals against Family Members
Family members of some draft evaders or national service deserters have been punished by fines of Nakfa 50,000 (US$3,333) and by detention, in a country with, according to the World Bank, per capita income in 2012 of $560.

Families are also punished when relatives living abroad fail to pay a 2 percent tax on foreign income, retroactive to 1992, or to contribute “national defense” fees. Punishments include revocation of resident families’ business licenses, confiscation of houses and other property, and refusal to issue passports to allow reunification of children and spouses with overseas parents or spouses.

Freedom of Expression and Association
The government maintains a complete monopoly on domestic sources of information since it closed all local press outlets in 2001 and arrested their staff. Telephone and Internet communications are monitored. Eritrea expelled the last accredited foreign correspondent in 2008. Although foreign language transmissions are accessible, the government jammed Al Jazeera in early 2013 and has long jammed overseas transmissions from Eritrea diaspora stations. At least six government journalists arrested in 2009 and 2011 remain in solitary confinement without trial.

No independent civil society organizations are permitted. Labor unions remain a government monopoly.

Key International Actors
Eritrea’s government has few allies. Relations with Ethiopia remain hostile following the 1998-2000 border war and Ethiopia’s failure to implement an international boundary commission’s ruling awarding disputed territory to Eritrea.

Eritrea has been under United Nations sanctions since 2009 because of its support for armed Islamic insurgents in Somalia and its refusal to release Djibouti prisoners of war captured during a 2008 invasion of Djibouti’s border territory.

A UN monitoring group reported in July 2013 that although Eritrea had made a tactical decision to court the Somali government, it fostered regional destabilization by “maintain[ing]close links to a network of warlords and other spoilers in Somalia,” including at least two Al-Shabaab leaders. Eritrea refuses to acknowledge that it holds Djibouti prisoners of war although three escaped in late 2011. Following the report, the UN Security Council retained sanctions and renewed the monitoring group’s mandate for a year.

Eritrea’s relationship with Qatar, which had been mediating Eritrea-Djibouti border issues, frayed in 2013 and Qatar apparently stopped funding a large Red Sea resort. The Yemeni Foreign Ministry complained that Eritrea seized Yemeni fishing vessels in international waters and detained their crews. In October, Eritrea released 81 Yemeni fishermen held for 18 months without trial; Yemen claims another 519 remain jailed.

In June 2013, Canada expelled Eritrea’s Toronto consul for continuing to solicit “national defense” fees (and the 2 percent tax) from Eritrean expatriates despite Canadian demands that he stop because the practice violated UN sanctions.

Eritrea has warmer relations with China. The Chinese government provided a 630 million Yuan ($10.3 million) loan in 2013 to construct canning, food cold-storage, and PCV pipe manufacturing plants. The projects will be run by SFECO, a Shanghai Construction Co subsidiary. SFECO bought a 60 percent share of the Zara gold exploration site near Asmara in 2013 and has contracts to repair and enlarge Asmara’s power plant. Lengthy power shortages occurred in 2013.

In earlier years, Eritrea expelled all nongovernmental aid agencies. In 2013, the UN and Eritrea agreed on a four-year $188 million “cooperation framework.” The UN will provide $50 million and attempt to raise the remaining $138 million from donor countries for capacity building, food security, environmental improvements, and social services. Providing assistance presents “acute coordination challenges,” according to the UN Office for the Coordination of Humanitarian Affairs, because of “access restrictions on international staff” and the “absence of up-to-date information” from the government.

The Bisha mine, a major hard currency generator, was expected to earn less in 2013 as production shifted from gold to copper and copper prices fell. Eritrea issues no budget; government finances are opaque and secret. President Afewerki nevertheless complained in 2013 that “international organization” statistics (ostensibly referring to the World Bank and International Monetary Fund) “are based on speculation and aimed at serving vested political interests” and “should be dismissed.”
Image

http://www.hrw.org/world-report/2014/co … rs/eritrea

Image

In a recent article in Times of Malta about g@y couples adopting children, I discovered anew how pharisaical people’s ignorance and hypocrisy can be. One sentence reads: “Countries like Ethiopia had been closing doors on adoptions for Maltese because of fears that prospective single parents could be g@y.”

Ethiopians, renowned for their inability to govern themselves and for living in the second poorest country in the world despite being one of the richest in mineral resources like gold, potash, copper, platinum and natural gas, are closing doors on adoptions by Maltese parents because these might be h o – m o se x ua l.

A country ravaged by illiteracy, corruption, child prostitution and political instability still has the damnable effrontery to pontificate on the s e x u a l orientation of a few good souls willing to take starving Ethiopian foundlings into their care.

If this doesn’t win an award as one of the most banal acts of immorality ever to find its way into State policy, nothing will.

It is staggering that African nations only too willing to accept handouts and ‘aid’ from developed countries that endorse h om ose x ua lity will recoil in horror at one of their own being cared for by a g@y couple.

Those African politicians who are so morally bankrupt that they will boast of being on the take and even hold ‘briberyauctions’ do not have the right to stand in the way of individuals whose only failings are being g@y and wanting to give a few children a better life.

Man accused of spying for ESAT sentenced to four years in prisonMikiyas Nigatu of the Ethiopian Airports Enterprise’s Gambella Airport Security personnel, who was charged by the federal prosecutor for delivering sensitive information to the ESAT journalist named Fasil Yenealem for 4,460 Br is sentenced to four years in prison by the Federal High Court’s Fourth Criminal Bench on January 20, 2014.

Mikiyas who has failed to defend himself against a 10 page written document from his e-mail and three pictures from his cell phone has been giving various information to the ESAT television station which was deemed by the Ethiopian government as “a media outlet for the terrorist group Ginbot 7” The charge indicates that Mikiyas has provided information about foreign investors who were killed in the Gambella region and other very sensitive security related materials.

ፍትህ ለበቀለ ገርባ!
የእስር ጊዜውን ያጠናቀቀው አቶ በቀለ ገርባ አልተፈታም::
‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የማረሚያ ቤቱን ሃላፊዎች

በእስር ቤት የሚገኘው የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ በባለፈው እሁድ የእስራት ቅጣቱን አጠናቆ የነበረ እና መፈታት የነበረበት ቢሆንም እስካሁን ድረስ በእስር ቤት ነው የሚገኘው:: በቅርቡ ከጓደኞቼ ጋር ሆነን ቃሌቲ ሄደን አግኝተነው ነበር፡፡ አመክሮ ለማግኘት እንደ መስፈርት የሚወሰደው፤ በቆይታው ወቅት የነበረው ስነ ምግባር በበቂ ሁኔታ እንዳሟላ እንደተገለፀለት ነግሮናል፡፡

ወደ ማረሚያ ቤት ከመግባቱ በፊት ማእከላዊ ያሳለፋቸው 41 ቀናት ሲደመሩ ነው ባለፈው እሁድ መውጣት የነበረበት፡፡ ማእከላዊ በእስር የቆየባቸው ቀናት መያዝና እና አለመያዝ የማረሚያ ቤቱን አስተዳደር የይሁንታ ፈቃድ ማግኘት እንደሚያስፈልግ ተነግሮታል፡፡ በህጉ መሰረት ከሆነ ግን ማንም መፍቀድ ሳይጠበቅበት ሊደመርለት ይገባ ነበር፡፡ትላንት ይህን ጉዳይ ይዘው የማረሚያ ቤቱን ሃላፊዎች ለጠየቁ ቤተሰቦቹ ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የሚል ምላሽ ተሰጥቷቸዋል፡፡

በቀለን ለመጠየቅ የሚፈልግ በስራ ቀናት ጠዋትና ከሰዓት፤ በእረፍት ቀናት ደግሞ ጠዋት ብቻ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ዞን 2 ሄዶ ማግኘት ይችላል፡፡

ፍትህ ለበቀለ ገርባ!

60ኛው የ‹‹ድምጻችን ይሰማ›› በራሪ ወረቀት አቢይ ጽሁፍ እነሆ!
በጠንካራ ወኔ ዛሬም ጥሪያችንን እናስተጋባለን!!

የተከበራችሁ ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች ሆይ! ‹‹ሀይማኖታዊ መብታችን ይከበር!›› ስንል የምናደርገው ሰላማዊና ህዝባዊ ትግል ዛሬ ወሳኝ ምእራፍ ላይ ይገኛል፡፡ ይኸውም የምንገኝበት የእፎይታ ጊዜ ሊነሳ አጭር ግዜ በቀረበት በዚህ ሰዓት ሰላማዊ ትግሉ የተጀመረበት ሁለተኛ ዓመት የሚታወስበት ወቅት ላይ መድረሳችን ነው፡፡ ከፊታችን ጁሙዓ ጀምሮ ለሁለት ተከታታይ ሳምንታት ሁለተኛ ዓመት የሞላውን የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ሰላማዊ የ‹‹መብቴ ይከበርልኝ!›› ጥያቄ በተለያዩ ሰላማዊ እንቅስቃሴዎች መዘከር እንጀምራለን፡፡ በዚህ ሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ በዝምታችን ውስጥ አልፈው የሚያስተጋቡ ሰላማዊ እንቅስቃሴዎችን እናደርጋለን፡፡ የእፎይታ ጊዜው ዝምታ አንዱ የሰላማዊ እንቅስቃሴያችን መገለጫ ሆኖ ላለፉት 6 ወራት ቆይቷል፡፡ አሁን ደግሞ በዚህ የእፎይታ ጊዜው የመጨረሻ እድሜ ላይ የምናደርገው የሁለት አመቱን የሰላማዊ ጥያቄያችንን ሂደት የምናስታውስበት እንቅስቃሴ በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጪም ሰፊ የህዝብ ተሳትፎ እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡ በመሆኑም የሁለት አመት ጉዟችንን በምናስታውስበት ሂደት ሁሉም የሙስሊም ማህበረሰብ ከወዲሁ ዝግጅት እንዲያደርግ ‹‹ድምፃችን ይሰማ!›› ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ሰላማዊ እንቅስቃሴያችን ሰላማዊ ሆኖ በመጓዝ ሰላማዊነቱን ለማደፍረስ መንግስትና ህገ ወጡ መጅሊስ የሚሰነዝሩትን የስም ማጥፋት ዘመቻ፣ የሚያሴሩትን ሴራ ወጥመድና እና ህገ መንግስቱን ክፉኛ የሚሸረሽሩ ህገ ወጥ ተግባራት ሁሉ በአላህ ፈቃድ እያከሸፈ ዛሬ ላይ ደርሷል፡፡ ኢንሻላህ ወደፊትም በሀያሉ ጌታችን አላህ ፈቃድ የእምነት ነፃነታችን ተከብሮ በሀገራችን ፍትህን እንደምንጎናፀፍ እምነታችን ሙሉዕ ነው፡፡ ይህን የምንለው ሀያሉ ጌታችን አላህ የተበደለን የሚክስ፣ በህዝብ ላይ ግፍ የሚፈፅምን መሪ የሚያስተካክል አልያም የሚቀይር ሁሉን ቻይና ተመልካች በመሆኑ ነው፡፡ ጌታችን አላህ በተከበረው ቃሉ እንዲህ ይለናል ‹‹…… ምእመኖቹንም መርዳት በእኛ ላይ ተገቢ ሆነ፡፡›› (ቅዱስ ቁርዓን 30፡47)

ዛሬ ላይም ቆመን ለሚመለከተው ሁሉ የምናረጋግጠው እውነታ ትግላችን ከስሜታዊነት ርቆ በሀቅ ላይ የተመሰረተ መሆኑን ነው፡፡ ትግላችን ‹‹የሀይማኖት ነፃነታችን ይከበር! በገዛ ሀገራችን በሀይማኖታችን የሚፈፀምብን ግፍ ይቁም!›› ነው፡፡ ትግላችን ‹‹ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ በሀገሪቱ የሚገኙ እስር ቤቶች የህግ ታራሚዎች የሚቆዩበት ስፍራ መሆናቸው ቀርቶ የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ማሰቃያና ማጎሪያ ስፍራዎች እስኪመስሉ ድረስ እየተደረገብን ያለው ዓይን ያወጣ የመብት ረገጣና የህገ መንግስት ጥሰት ይቁም!›› ነው፡፡ ‹‹የህዝብን መብት እንዳሻቸው ረግጠውና የሀይማኖት ነፃነትን ነፍገው ሲያበቁ ይህን ፍፁም ህገ ወጥና ክፉ ስራቸውን ለመሸፈን በማሰብ በተቃራኒው በሚዲያ ቀርበው በየእለቱ ‹አክራሪ፣ አሸባሪ፣ ፅንፈኛ፣ ህገ መንግስቱንና የሌሎችን እምነት መኖር የማይቀበሉ› ሲሉ የሚያቀርቡት የተገላቢጦሽ ልፈፋና ድራማ ህዝብ አንቅሮ የተፋው እዚህ ግባ የማይባል ከንቱ ድካም መሆኑን ደግመው ይገንዘቡ›› ነው፡፡ ‹‹ለልማት መዋል የሚገባው የሀገር ሀብት እና ጊዜ የንፁሁን ህዝበ ሙስሊም ስም ለማጥፋት፣ የህዝበ ሙስሊሙን ሀይማኖታዊ ነፃነት እና ህገ መንግስታዊ መብትን ለመገደብ፣ ህዝብ በይፋ ያወረዳቸውን የመጅሊስ ሹመኞች ከህዝበ ሙስሊሙ ተቃራኒ ተሰልፈው እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ በማዋል ሀገርን ወደ ፊት ከማራመድ ይልቅ ወደ ኋላ የሚጎትት አካሄድ ላይ መጠመድ ይቁም!›› ነው ጥያቄያችን፡፡ ‹‹እነዚህ ሁሉ ህገ ወጥ ድርጊቶች ቆመውና ጥፋተኞችም በፍትህ ፊት ታርመው የጠየቅናቸው ሰላማዊና ህገ መንግስታዊ ጥያቄዎች ይመለሱልን!›› እንጂ ሌላ አልነበረም ጥያቄያችን፡፡

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እነኚህን ሁሉ ለግርግር የሚጋብዙ ህገ ወጥ ድርጊቶች እና በደሎችን በእልህ አስጨራሽ ትእግስትና ፅናት ተሻግረው ዛሬ ላይ ደርሰዋል፡፡ ይህን ያደረግነው ከምንም ነገር በላይ ዲናችን የሚያስተምረንን ሰላማዊነት ለማንፀባረቅ መሆኑን መገንዘብ ያሻል፡፡ እንዲሁም በተመሳሳይ ምንም እንኳ ለሀገር ሰላም እና ለህዝብ ደህንነት መጨነቅ ያለበት አካል በተቃራኒው ተሰልፎ የህዝብን ሰላም እና የተረጋጋ ህይወት፣ እንዲሁም የሀይማኖት እና የግለሰብ ነፃነቶችን በሚያደፈርሱ ተግባሮች ላይ ሲጠመድ ብናስተውልም ነገር ግን እንደ ህዝብ ለሀገራችን እና ለህዝቦቿ መረጋጋት በማሰብ፣ ለሰላሟ እና ደህንነቷ በመጨነቅ፣ በሰከነ ልቦናና በተገራ የሀላፊነት ስሜት እልህ የሚያስጨርሱ ክስተቶችን በሚያስደንቅ ፅናት፣ አንድነት እና ትእግስት አልፈናል፡፡ ይህ እንደ ህዝብ በአላህ እገዛ የተቸርነው ፀጋ ነውና አልሐምዱሊላህ!!

የእፎይታ ጊዜውም ቢሆን የተቀመጠበት ዋነኛ ዓላማ ይህንኑ ከግንዛቤ በማስገባት መንግስት ከስሜታዊነት ወጥቶ በሰከነ መንፈስ ለተፈጠሩት ችግሮች መፍትሄ እንዲያስቀምጥ የማሰቢያ እና የማሰላሰያ ጊዜ መስጠት ነበር፡፡ በተመሳሳይ ‹‹ተቃውሞ ቢቆምና ሙስሊሙ ዝም ቢል መንግስት ምን ሊያደርግ እንደሚችል በተግባር በማየት ማረጋገጥ›› የሚሉና መሰል ዓላማዎችም ነበሩት፡፡ በመሆኑም መንግስት በዚህ የእፎይታ ጊዜ ከፈፀመው ስህተት ከመመለስ ይልቅ በዚያው የስህተት መስመር መጓዙን እንደቀጠለ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ ተቃውሞ የሌለበት አየር ቢመጣም እንኳ እስሩ፣ ድብደባው፣ እንግልቱ፣ የኢማሞች መባረርና መንግስታዊ ኢማሞች መተካቱ፣ የመስጂድ ነጠቃው፣ የሀሰት ክሱና የሀሰት ፍርዱ ሁሉ እንደሚቀጥሉ እንጂ እንደሚቆሙ የእፎይታ ጊዜው አላሳየንም፡፡

በመሆኑም በዚህ የእፎይታ ጊዜው የመጨረሻ እድሜ ላይ የትግላችንን የሁለት ዓመት ጉዞ ስናስብ በሙሉ መነቃቃት ላይ በመሆን ነው፡፡ በጠንካራ ወኔ ዛሬም ጥሪያችንን እናስተጋባለን፡፡ ዛሬም እንደ ትላንቱ ሁሉ ለዲናችን መከበር ዘብ በመቆም ሀይማኖታዊ ነፃነታችንን እስክንጎናፀፍ እና የፈጣሪያችንን አምልኮተ ህግጋቶች እንዳንተገብር፣ ብሎም እንድንርቅ በማሰብ የሚደረጉብን ጫናዎች እስኪቆሙ ድረስ ሰላማዊ ሆነን ከመታገል አንወገድም፡፡ ዛሬም አንድነታችን እንደጠበቅን ለዲናችን መከበር ያለንን ጠንካራ ወኔ አጉልተን እናሳያለን፡፡ ሂደታችን ሰላማዊና ከግብታዊነት የራቀ፣ ሀይማኖታዊ መብት እንዲከበር የመጠየቅ ሂደት ነውና የጠየቅነው መብት እስኪከበር በተለያዩ ሰላማዊ መንገዶች መታገላችንን እንቀጥላለን፡፡

የምንከፍለው መስዋእትነት ለዲናችን መሆኑን ጠንቅቀን መረዳታችን በሰላማዊ ትግሉ ላይ አላህ ወፍቆን በምንከፍለው መስዋእትነት ሳቢያ የምናገኘውን ደረጃ ማሰብ ምንኛ የሚያጓጓ ፀጋ መሆኑን ግፍ የሚፈፅሙብን አካላት በጥልቀት እንዲረዱት ደግመን የምናስመሰክርበት ሂደት ላይ ነን፡፡ ውድ ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች! ከኛ የሚጠበቀው ዲንን በመጠበቁ ሂደት ላይ ሁሉም በሚችለው አቅም መረባረብ ነው፡፡ ይህን ስናደርግ ውስጣችን በሚከተለው የሀያሉ ጌታችን አላህ ቃልኪዳን ይረጋጋል፡-

‹‹እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን (ሀይማኖቱን) ብትረዱ ይረዳችኋል…›› (ቅዱስ ቁርዓን 47፡7)

አዎን! እስልምናችንን ለመጠበቅ በምናደርገው እያንዳንዷ እንቅስቃሴ ያለጥርጥር የአላህ አርዳታ ከጎናችን ይሆናል፤ በንፁህ ልቦና በአላህ መንገድ ላይ እስከቆምን ድረስ፡፡ አላህ ባዘዘው መንገድ ላይ መቆም ምንኛ መታደል ነው!!

በሌላ መልኩ ለዲናችን የምንከፍለው እያንዳንዱ መስዋእትነት ዋጋው አላህ ዘንድ እንጂ የትም አይደለም፡፡ ሺዎች ታስረናል፤ አልያም የግፍ በትር አርፎብናል፡፡ ከእስር የተረፉ ብዙ አሊሞቻችን፣ ዱዓቶቻችን እና ወጣቶቻችን ተሰደዋል፤ ተወልደው ካደጉባት፣ ኖረው ከከበዱባት የገዛ ሀገራቸው ሰላምን ፍለጋ እንዲሰደዱ ተገደዋል፡፡ ወጣት አዛውንት፣ ወንድ ሴት ሳይለይ የከፈልናት እያንዳንዷ መስዋእትነት ጌታችን ዘንድ ተመዝግባ ለምንዳ ትቀመጣለች፡፡ አዎን! ዛሬን ስለ ዲኑ እና ህብረተሰቡ በመቆርቆር፣ ሀቅን በመናገር፣ ሙስሊሞችን ወደ አንድነት በመጣራት ጊዜውን ያሳለፈ ወጣት ነገ ጌታው ዘንድ ትልቅ ክብርን ይጎናፀፋል፡፡ ጌታችን አላህ በተከበረው ቃሉ እንዲህ ይላል፡-

‹‹… እነዚያም የተሰደዱ፣ ከአገሮቻቸውም የተባረሩ፣ በመንገድም የተጠቁ (በአላህ መንገድ ላይ ግፍ የተፈፀመባቸው)… ክፉ ስራዎቻቸውን በእርግጥ አብሳለሁ፤ በስሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በእርግጥ አስገባቸዋለሁ፤ ከአላህ ዘንድ የሆነን ምንዳ (ይመነዳሉ)፤ አላህም እርሱ ዘንድ መልካም ምንዳ አለ፡፡›› (ቅዱስ ቁርዓን 3፡195)

ዛሬም አንድነታችንን እንደጠበቅን ለዲናችን መከበር ያለንን ጠንካራ ወኔ አጉልተን እናሳያለን!! የፈጣሪያችንን አምልኮተ ህግጋቶች እንዳንተገብር ብሎም እንድንርቅ በማሰብ የሚደረጉብን ጫናዎች እስኪቆሙ ድረስ ሰላማዊ ሆነን ከመታገል አንወገድም!! ድልም ከአላህ እንጂ ከሌላ አይደለምና!

ድምጻችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

ሽንፈትን መቀበል ትልቅ ፀጋ ነው፡፡ ሽንፈትን ለመቀበል ዝግጁ የሆነ ሲያሸንፍ ጉራ አይነዛም፡፡ንቅዘት ብቻ ነው ጉዞው፡፡ የዓለም ታላቅ ኃይለም ያሸንፍ አገራዊ ኃይል፤ በምን ሁኔታ አሸነፈን እንጂ፤ አልሸነፍም ማለትን መመርመር አለብን፡፡ የማረከውን ሰው በሰብዓዊ መንገድ ለመያዝ የሚችል ተዋጊ ጀግንነትን ከጭካኔ በመለስ ማየት አይሳነውም፡፡ ምህረት ለማድረግም ፍርሃትና ሥጋት አይኖርበትም፡፡ “የተጠማ ከፈሳሽ፣ የተበደለ ከነጋሽ” የሚለው ምሣሌያዊ አነጋገር በቀላሉ ይገባዋል፡፡ ምርጫ፣ በተለይም በአገራችን፣ በሚካሄድበት ጊዜ የሚያጋጥመን የአንድ ሣንቲም ሁለት ገጽ፤ 1ኛ/ የተሸናፊው ሽንፈትን አለመቀበል እና 2ኛ/ የአሸናፊው ዘራፍ ባይነት ነው፡፡ ይህ ማለት ከምርጫው በኋላ አሸናፊና ተሸናፊ አይጥና ድመት ናቸው ማለት ነው፡፡ በዲሞክራሲያዊ ዐይን መተያየት ቀርቶ እንደ ዜጋ መተሳሰብም ይቀራል፡፡ “የማትወልደውን ሶሻሊዝም ሲያማምጡዋት፤ ከነ ካፒታሊዝሟም አስወረዳት!” እንደተባለው ነው፡፡ አዲስ ሥርዓት መፍጠር ቀርቶ አሮጌውንም ማጣት አለ፡፡ ቁልቁል ማደግ የሚባለው ዓይነት!

ዲሞክራሲ በምርጫ ሳጥን ብቻ ሳይሆን፤ በኑሮአችን ድርና ማግ ውስጥ ሁሉ የሚኖር መሆን አለበት፡፡ ሁሉን ጐራሽ የሆነ አሠራር ከተከተልን ፖለቲካውም ሆነ ባህሉ ልሙጥ ይሆናል፡፡ ይህም ህዝብን ሽባ ያደርገዋል፡፡ ከዚህ ይሰውረን፡፡ ሥልጣንን ማጋራት፣ ሥራን ማከፋፈል ይቻለን ዘንድ ትምህርታችንን ይግለጽልን! የችግር ጊዜ ሁኔታዎች ይለዋወጣሉ፡፡ የላዩ ታች የታቹ ላይ ቦታ ሊቀይር ይችላል፡፡ በደስታው በተድላው ጊዜ የሚደረገው ሁሉ ይቀራል፡፡ ድህነት ጥላውን ሲጥል ማጀት ጓዳው መራቆቱ ብቻ ሳይሆን አስተሳሰብም ይራቆታል፡፡ ዕምነት ይመነምናል፡፡ ጀግንነት ይኮሰምናል፡፡ ቆራጥነት ይከሳል፡፡ የሌለው ላለው ያድራል፡፡ ተገዢ ገዢውን ከልኩ በላይ እጅ ይነሳል፡፡ አድር ባይነት የዕለት የሠርክ ጉዳይ ይሆናል፡፡

ሁሌ በተለመደው የፖለቲካ መንገድ መሄድ ለህዝብ ዕድል አይሰጥም፡፡ ሌላው ይቅርና ለፖለቲከኛው ለራሱም ዕድል አይሰጥም ፡፡ እስከንቅዘት ብቻ ነው ጉዞው፡፡ ወደ አዲስ አይን መክፈት አያመራም፡፡ የትኛውም ዘመን በየትኛውም ፓርቲ አንድና አንድ መንገድ ብቻ ልከተል ባለ ሰዓት የሚከሰት ችግር ነው፡፡ የታየ፣ የተረጋገጠ ጉዳይ ነው!! “እወርካ ሥር የገደለ፣ ዘወትር እወርካ ሥር ያደፍጣል” የሚባለው እንዲህ ሲሆን ነው! ጦርነት ሰልችቶናል፡፡ ከዚህ ቀደም በተካሄደው ጦርነታችን ብዙ ሰው አልቆብናል፡፡ ብዙ ንብረት ወድሞብናል፡፡ ኢኮኖሚያችን ደቅቋል፡፡ ስለዚህ ሌላ ጦርነት ይጎዳናል እንጂ ምንም አይፈይደንም!

እንቢኝ ለመብቴ እንታገላለን ያሉት የደሴ ሙስሊሞች ደሴን በበራሪ ወረቀት አሸብርቀዋት አደሩ::

መንግስት የደሴን ሙስሊም በሀይል ቀጥቅጨ ተቆጣጥሬዋለሁ ብልም ፉከራውን መና የሚያሰቀር ሁኟን:: በተያያዘ ዜናም በዚሁ ድርጊት የተደናገጡት የመንግስት ደህንነቶች እና አቀንቃኝ ካድሬወች በሌሊቱ ተነስተው በስራ ተጠምደው እንዳደሩም ለማወቅ ተችሏል::

በበራሪ ወረቀቱ ላይ ጎልተው ከሚታዩት መፈክሮች መካከል 1.ኮሚቴወቻችን ወንጀለኝ አይደሉም ንፁህ ናቸው ይፈቱልን 2.መንግስት በሙስሊም እና ክሪስቲያን መካከል ግጭት ለመፍጠር ድራማ እየሰራ በ Etv የሚያቀርበው ፕሮፓጋንዳ ይቁም 3.አሸባሪ አይደለንም 4.ትግሉ ይቀጥላል 5.ድምዻችን ይሰማ እና ኮሚቴው በፍጥንነ ትይፈታ አለያ አንደራደርም የሚሉት ይገኙበታል::

የደሴ ሙስሊም በኮሚቴወቹ ላይ መንግስት የጥፋት እጁን ከሰነዘረ እንደማይደራደሩ ዛሬ ተበትኖ ባደረው 50000 ሺ በራሪ ወረቀት አስረግጦ አሳስቧል:: ሲቀጥልም ዱላ እስር እና ግድያ የማይበግረው የደሴ ሙስሊም ትግሉ እስከ ድላችን ድረስነው በቀይ ይሰመርበት ሲሉ አሳስበዋL:: ድል ፍትህ ለተጠማው ሙስሊም አላህ አክበር!

ኢትዮጵያ እያካሄደችው ያለው ግንባታ ማንኛውንም ዓይነት ሕግ የጣሰ አይደለም በማለት መንግሥት የግብፅን አቤቱታ ውድቅ አድርጓል፡፡

አል ሞኒተር የተባለ የግብፅ ሚዲያ የተለያዩ የአገሪቱ ባለሥልጣናትን በመጥቀስ፣ ግብፅ በኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ላይ ያላትን ተቃውሞ ዓለም አቀፍ ማድረግ እንደምትፈልግ ዘግቧል፡፡

‹‹የህዳሴው ግድብ አሁን ባለው የግንባታ ደረጃ ተገንብቶ ዕውን የሚሆን ከሆነ በግብፅ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ከባድ ነው፡፡ በመሆኑም ጉዳዩን ወደሚመለከታቸው ዓለም አቀፍ ተቋማት መውሰድ እንደሚገባ፣ ለዚህም አስፈላጊው ዝግጅት እየተደረገ ነው፤›› ያሉት የአገሪቱ የመስኖና ውኃ ሀብት ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ካህሊድ ዋሲፍ ናቸው፡፡

‹‹ግብፅ የህዳሴው ግድብ ግንባታን ፈፅሞ አትፈቅድም፡፡ ይህንን ለማሳካትም ኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የውጭ ዕርዳታ ለግድቡ እንዳታገኝ ግፊት እናደርጋለን፤›› ሲሉ በይፋ ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ የኢትዮጵያን ግድብ በማውገዝ ከግብፅ ጐን እንዲቆም አስፈላጊው ጥረት እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ በዓለም አቀፍ ሕግ የተከበረና የተረጋገጠ መብት አላት፡፡ ነገር ግን ይህ የግብፅ መብት በኢትዮጵያ እየተጣሰ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ ሕጋዊ መብት አላት የሚሉት ቃል አቀባዩ፣ ማናቸውም የተፋሰሱ አገሮች ተፋሰሱን በመጠቀም ወደ ልማት መግባት ሲፈልጉ በቅድሚያ ግብፅን የማማከርና ይሁንታ የማግኘት ግዴታ አለባቸው ሲሉ የአገራቸውን አቋም አስታውቀዋል፡፡

ኢትዮጵያ ይህንን ግዴታ በመጣስ የህዳሴውን ግድብ ግንባታ መጀመሯ በራሱ ሕግን የጣሰ መሆኑን፣ ነገር ግን የግብፅ መንግሥት ጉዳዩን በወዳጅነት በመያዝ ሲወያይ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የህዳሴው ግድብ ግንባታ ምንም ዓይነት ጉዳት በግብፅ ላይ እንደማያደርስ ኢትዮጵያ ለማረጋገጥ እንቢተኛ በመሆኗ ግብፅ ከውይይቱ ራሷን እንዳገለለች አስረድተዋል፡፡

የግብፅ የቀድሞ የመስኖና የውኃ ሀብት ሚኒስትር ሙሐሙድ ናስር አል ዲን አላም በበኩላቸው፣ ግብፅ ከዚህ በኋላ በህዳሴው ግድብ ላይ ሌላ አማራጭ የላትም ብለዋል፡፡ የቀረውና በፍጥነት ተግባራዊ መሆን የሚገባው አማራጭ ጉዳዩን ዓለም አቀፋዊ ይዘት እንዲኖረው ማድረግ፣ በዋናነትም ይፋዊ ቅሬታና ተቃውሞ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ማቅረብ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹‹ማንኛውም የዓባይ ተፋሰስ ተጋሪ አጋር በወንዙ ላይ ፕሮጀክት ከመጀመሩ በፊት የግብፅን ይሁንታ ማግኘት አለባት የሚለው ስምምነት ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት ያለው ነው፤›› በማለት የሚከራከሩት የቀድሞው ሚኒስትር ኢትዮጵያ ይህንን ስምምነት በመጣስ ለጀመረችው ግንባታ በተባበሩት መንግሥትት ድርጀት ልትጠየቅ ይገባታል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል አሁን ያለውን አለመግባባት በተመለከተም ዓለም አቀፍ እውነት አፈላላጊ ኮሚቴ ተቋቁሞ ማጥናት ይኖርበታል በማለት ተከራክረዋል፡፡

የግብፅ ባለሥልጣናት እያንፀባረቁት ስላለው አዲስ አቋም የተጠየቁት የኢትዮጵያ የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር የድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፈቅ አህመድ፣ ‹‹ኢትዮጵያ የቅኝ ግዛት ውል አይመለከታትም፣ ምክንያቱም አልፈረመችም፤›› ሲሉ የግብፅ ባለሥልጣናት መግለጫን አጣጥለዋል፡፡ የቅኝ ግዛት ውሉ የተፈረመው በግብፅና በእንግሊዝ መካከል መሆኑን ያስታወሱት አቶ ፈቅ፣ እንግሊዝ ቅኝ የገዛቻቸውን ኬንያ፣ ታንዛኒያና ኡጋንዳ በመወከል ስምምነቱን ፈርማለች፡፡ ይህ ግን ኢትዮጵያን ፈፅሞ አይመለከትም ብለዋል፡፡

የግብፅ የቀድሞው የመስኖና የውኃ ሀብት ሚኒስትር በተደጋጋሚ ይህንን መሳይ ነገር ያነሳሉ በማለት ያስታወሱት አቶ ፈቅ፣ ‹‹ሰውዬው ከሳይንስ ውጭ ነው የሚናገሩት፣ ከእሳቸው የሚጠበቅ አይደለም፤›› ሲሉ ወቅሰዋቸዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ የጀመረችው የህዳሴው ግድብ ግንባታ የትኛውንም ዓለም አቀፍ ሕግ የጣሰ አይደለም፡፡ ወደፈለጉበት ቢሄዱ የሚመጣ ነገር የለም፤›› ሲሉ አክለዋል፡፡ ጉዳዩን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ መምራት ሊያተርፍ የሚችለው በሁለቱ አገሮች ያለውን የትብብር መንፈስ ማጥፋት ነው ሲሉ የግብፅ ባለሥልጣናትን የሰሞኑን ዘመቻ አውግዘዋል፡፡ Reporter

ከኡጋንዳ ኢንቴቤ ተነስቶ ወደ ሰንዓ የመን በመብረር ላይ የነበረ ንብረትነቱ የዩክሬን የሆነ አንቶኖቭ 28 የመንገደኞች አውሮፕላን ባለፈው ሰኞ አዲስ አበባ አቅራቢያ ለገዳዲ አካባቢ ተከሰከሰ፡፡

ከኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ የአውሮፕላኑ አብራሪዎች ሰኞ ማለዳ ከባለሥልጣኑ ጋር ባደረጉት የሬዲዮ ግንኙነት ከኢንቴቤ ተነስተው በኢትዮጵያ በኩል ወደ የመን ለመብረር ፈቃድ ጠይቀው ነበር፡፡ ባለሥልጣኑም የበረራ ፈቃድ ሰጥቷቸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ኤር ናቪጌሽን ክፍል ለአብራሪዎቹ የሚበሩበትን ከፍታ ሰጥቷቸዋል፡፡ አውሮፕላኑ የኢትዮጵያን አየር ክልል አቋርጦ በማለፍ ላይ ሳለ አዲስ አበባ አካባቢ ሲደርስ የሞተር ብልሽት ያጋጥመዋል፡፡ ይህንኑ ለአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የበረራ መቆጣጠሪያ ማማ አሳውቆ ‹‹ኢመርጀንሲ ላንዲንግ›› እንደሚያደርግ (በድንገተኝነት እንደሚያርፍ) ሪፖርት አድርጐ፣ ከጠዋቱ 3፡35 ሰዓት ላይ ለማረፍ ወደ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በማምራት ላይ ሳለ ለገዳዲ አካባቢ ተከስክሷል፡፡

አደጋው እንደደረሰ የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ፈልጐ ማዳን ቡድን ወደ ሥፍራው ተንቀሳቅሶ የአውሮፕላኑ አብራሪዎችን ወደ ሆስፒታል በመውሰድ ሕክምና እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ በአውሮፕላኑ ውስጥ ተሳፋሪዎች እንዳልነበሩ ታውቋል፡፡ በአደጋው አብራሪዎቹ የተጐዱ ቢሆንም፣ ሕይወቱ ያለፈ ሰው እንደሌለ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን የአውሮፕላን አደጋ መከላከልና ምርመራ ክፍል ባለሙያዎች የአደጋውን መንስዔ ለማወቅ ምርመራ ጀምረዋል፡፡ ባለሙያዎቹ አውሮፕላኑ ወደ ወደቀበት ሥፍራ በማምራት መረጃ በማሰባሰብ ላይ ይገኛሉ፡፡

ሩሲያ ሰራሽ የሆኑ አንቶኖቭ አውሮፕላኖች ከተመረቱ ረዥም ጊዜ ያስቆጠሩ በመሆኑ በየጊዜው እክል እየገጠማቸው በተለያዩ አገሮች በመከስከስ ይታወቃሉ፡፡ እነዚህ ዕድሜ ጠገብ አውሮፕላኖች ዋጋቸው ርካሽ በመሆኑ በአፍሪካ አገሮች በብዛት ይገኛሉ፡፡ ያረጁ በመሆኑና ተገቢ የሆነ ጥገና ስለማይደረግላቸው በተለያዩ የአፍሪካ አገሮች በተደጋጋሚ አደጋ እንደሚያደርሱ የአቪዬሽን ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡ Reporter

በምስራቅ ሃረርጌ ከ59 ሰዎች በላይ መገደላቸውን መንግስት ግጭቱን ሆን ብሎ መቀስቀሱን የኦሮሞ ጥናት ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኢብራሂም ገለጡ:: የማህበሩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኢብራሂም ኢሌሞ ለኢሳት እንደገለጹት ባለፉት ጥቂት ወራት በአንያ፣ ማቶ እና ሙለቄ ቆላማ ወረዳዎች ላይ በፌደራል መንግስቱ እውቅና የተቋቋመውና ስልጠና የሚሰጠው ልዩ ሚሊሺያ እየተባሉ የሚጠሩት ሃይሎች በኦሮሞዎች ላይ በሰነዘሩት ጥቃት 59 ገድለው፣ 42 አቁስለዋል፤ ጉዳት ከደረሰባቸው መካከልም ሴቶችና ህጻናት ይገኙበታል።

“በድንበር አካባቢ የሚኖሩ ህዝቦች ሰላም ካገኙ ለተቃዋሚዎች ምቹ ቦታ ሊፈጥሩ ይችላል በሚል እሳቤ የሁለቱን ክልል ህዝቦች እያጋጨና እርስበርስ ተጠባብቀው እንዲኖሩ ለማድረግ ” መንግስት ግጭቱን ሆን ብሎ መቀስቀሱን የገለጡት ዶ/ር ኢብራሂም ፣ በግጭቱም እድሜውን ለማራዘም እንደሚያስብ ተናግረዋል። ማህበሩ ለአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ፣ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና ለሌሎችም አገራት ደብዳቤ ማስገባታቸውን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል ። ኢሳት ዜና

ምንሊክ ሳልሳዊ
እኛ ሃገራችንን የምንወድ ኢትዮጵያን ስለ ፖለቲካ ድርጅቶች አያገባንም::እንዲያድጉ እንዲለሙ እንዲመነደጉ እናበረታታለን እንጂ በነዙ ስትራቴጂ አልባ ድፍን ደረቅ ፖለቲካ ውስጥ ገብተን አብረን በጭቃቸው መቡካት አንፈልግም::የወደደ ይውደድ የጠላ ይጥላ እትዮጵያ ውስጥ ወያኔን ጨምሮ ሁሉም የፖለቲካ ጎራ ጥያቄው የስልጣን እና የአገዛዝ ሩጫ ነው::የእኛ የዜጎች ጥያቄ ግን ፍትህ መልካም አስተዳደር የአገልግሎት አቅርቦት እና ሰላም ነው::

ወያኔ የሚያደፈርሳቸው ተቃዋሚ ነን የሚሉትም በአቅማቸው የሚያደፈርሷቸው ሰላሞቻችን ይመለሱልን::ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያን የሚበጅ አስተዳደር ለማምጣት መጀመሪያ የህዝቦች ጥያቄ መመለስ የለውጥ እርምጃ መምጣት አለበት::
ለዘላቂ ልማት እንሰራለን በሚል ስርኣት ውስጥ የመሰረታዊ የዲሞክራሲ መብቶች በጊዜያዊነት መኖር እና እንደመነገጃ መጠቀም ህዝብን አገለግላለሁ ሳይሆን አጭበረብራለሁ እንደማለት ይቆጠራል:: የወያኔ ስርኣት ባለስልጣናት በፍርሃት ተውጠው በሚኖሩባት በዚች ኢትዮጵያችን የፍትህ እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ አሁንም እጅግ መልስ የሚያሻቸው ጉዳዮች ናቸው::ዜጎች በሃገራቸው እንዳይኮሩ በመኖር ደህንነታቸው ላይ ጥርጣሬ እንዲያሳድሩ እየተደረገ ስለሆነ ይህ ደሞ ወያኔ በዘላቂነት የያዘውን ስልጣን ላለመነጠቅ የሚሰራው ፖለቲካዊ ደባ ውጤት መሆኑ እሙን ነው::

ፍትህን እና መልካም አስተዳደርን ወደ እውነት ያመጡ ህጎች በኢትዮጵያ አሉ የሚለው ወያኔ ህዝቦች ግን በተግባር ተጠቃሚ ሲሆኑ አላየንም::ህጎቹ በተግባር ይዋሉ ይህንን ህጎች በመመሪያ በደብዳቤ እና በስልክ የሚቀይሩ የሚደፈጥጡ በጥቅም የሚሸጡ የሚረጋግጡ የሚለውጡ ከየወንበራቸው ተሽቀንጥረው ይጣሉ:: የቀን ተቀን የፍትህ እና የመልካም አስተዳደር ሂደት ውስጥ እጃቸውን እያጠለቁ ፍትህን የሚያዛቡ አስተዳደራዊ በደሎችን የሚፈጽሙ ባለስልጣናት የህዝብን ማህበራዊ ህይወቶች ከማፋለሳቸውም በላይ ፖለቲካው እንዲጭበረበር ኢኮኖሚው እንዲደቅ ሃገር በብድር እንድትዘፈቅ ህዝብ እንዲደኽይ ከባዱን ሚና እየተጫወቱ ነው::

ህዝቦች ህግ እየጸደ ህግ እየተሽሞነሞነ እና እየተብለጨለጨ ቢቀመጥ ምንም የሚጠቅማቸው ነገር እንደሌለ መታወቅ ያለበት ሲሆ አንድ ህዝብ ባላረቀቀ ባልተወያየበት እና ባላጸደቀው ህግ እየተገዛ ፍትህን እና መልካም አስተዳደርን እንዴት ማስፈን ይቻላል??? መተማመን እና የዜግነት ኩራቱን በሚሰብሩ ባለስልጣናት እየተሰበረበት ያለ ህዝብ ፍትህን እና አስተዳደራዊ እንዲሁም አገልግሎቶችን በተግባል ለማየት እና ለመጨበጥ አልቻለም:: ለተበደለና ፍትሕ ላጣ ዜጋ፣ መልካም አስተዳደር አጥቶ ለሚንገላታ ዜጋ ፍትሕና መልካም አስተዳደር እንዲኖር በአንቀጽ ተደንግጓል እያልን ብናወራ ዋጋ የለውም::

ህዝብ ባለው ስርኣት ላይ እምነት የለውም:; ይህ ደግሞ ራሱ ስርኣቱ ያረጋገጠው ነገር ነው ኢትዮጵያውያን የስርኣቱ ታጣቂ ሃይሎች በሌሎች ወገኖቻቸው ላይ የሚያደርሱትን የሰብኣዊ መብት ጥሰት እያዩ በሃገሪቱ ህግ የለም እኔም ነገ እደበደባለሁ እታሰራለሁ ንብረቴን እነጠቃለሁ መብቴን እነፍርጋለሁ እጠቃልሁ እገደዳለሁ እሰደዳለሁ እገደላለሁ በሚል በስርኣቱ ላይ ያላቸው እምነት የተሟጠጠ ከመሆኑም በላይ ከትንሽ እስከ ትልቅ ከሃገር የመውጣት ንብረትን እና ሃብትን የማሸሽ ተግባር ላይ በመሰማራት በዜግነት አለመተማመን እንዲፈጠር በሩን በርግዶ ከፍቷል ይህ ደሞ ህጎች በተግባር ህዝብን አለማገልገላቸው እና በባለስልጣናት የመደፍጠጣቸው ውጤት ነው::

በተግባር ፍትህን እና መልካም አስተዳደርን እውን ለማድረግ በቁርጠኝነት የተነሳ ማንም የለም::ስርኣቱም በጥቅመኞች የሚመራ ህዝቡም ላላወጣው ህግ በዝምታ ደንታቢስነቱን እየገለጸ ነው; ፍትህን እና መልካም አስተዳደርን የሚጥስና የሚያደናቅፍ የስርኣቱ ባለሥልጣን፣ ዜጋም ሆነ ግለሰብ፣ በማስረጃ ሲታይና ሲረጋገጥ ዕርምጃ ለመውሰድ ሕግ ፊት ለማቅረብ ምንም አይነት የተሰራ ስራ ካለመኖሩም በላይ በባሰ መልኩ በይፋ ህጎች ሲደፈጠጡ እያየን ነው:: ባለሥልጣንም ሆነ ባለ ሀብት፣ ታዋቂም ይሁን ተራ ዜጋ፣ ከፈለገው ብሔር ብሔረሰብ ይምጣ፣ የፈለገውን ሃይማኖት የሚከተል ይሁን፣ የጾታና የዕድሜ ልዩነት ሳይኖር ተቃዋሚም ይሁን ደጋፊ ሁሉም ሕግ ፊት፣ ፍትሕ ፊት፣ መልካም አስተዳደር ፊት እኩል መሆኑን አምነን በተግባር ለማዋል ቁርጠኝነት በፍጹም የለም:: ፍትህ እና መልካም አስተዳደር እንዴት ሊረጋገጡ ይችላሉ በዚህ ሁኔታ ውስጥ እየተጓዝን ነው ጥያቄያችን ;ስለዚህ ህዝብ ለውጥ ይፈልጋል::

ምንሊክ ሳልሳዊ አገር በኔ ብቻ ተመርታ አገር አትሆንም ብሎ፤ ኃይለኛውና አሸናፊው ከወጣበት መሠላል ዝቅ ብሎ፤ ግማሽ መንገድ ወርዶ እንነጋገር፣ እንወያይ የማለት ባህል፤ ተሸናፊውም ከቁጭቱ፣ ከቂሙ፣ ለመጣል እንጂ አብሮ ለመቀመጥ አልፈልግም የሚልበትን ግትር አቋም ትቶ፤ እኔም የሀገር ጉዳይ ያገባኛል፣ “እንድትሰፉ እንጂ እንደትጠፉ አልፈልግም” ብሎ፤ መንገድ መሻት ያሻዋል፡፡

ቤት ንብረት በሀራጅ ከሚያስሸጥ ድህነት ይሰውረን፡፡ በሎተሪ ከሚያሳምን የገጠመኝ ዘመን ያውጣን፡ ከሁሉም በላይ ግን ለመለመን እንኳ ጥቂት የራስ መንቀሳቀስ እንደሚያሻን መገንዘቢያ የሚሆነን ልብ ይስጠን!!በሀገራችን ከድህነት እኩል የሚፈታተነን ችግር፤ ቢያንስ ግማሽ መንገድ እንኳ ሄዶ ለመደራደር ዕውቀቱን፣ ጥበቡን አሊያም ቀና ልቡናውን ማጣታችን ነው፡፡ ግማሽ መንገድና የመቻቻል፣ ልዩነትን የማስተናገድ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን የመልመድ ትልቅ ፀጋ ነው፡፡

የኋላ ታሪክ የሌለው የሚያውቀው ዛሬን ብቻ ነው፡፡የአንድ ቀን ታሪክ የሌለው የሚያውቀው ዛሬን ብቻ ነው፡፡ አንድ ቀን ባዶነት መሰማቱ አይቀርም፡፡ ከሌላ አካል ተከፍሎ መፈጠር ዕድሜ ልክ ሙሉነት ሳይሰማን እንድንኖር ማድረጉ አሌ አይባልም፡፡ ራስን ችሎ፤ በራስ ተማምኖ ለመኖር ራስን ሆኖ መፈጠርን ይጠይቃል፡፡በሀገራችን በፖለቲካ መከፋፈል እንጂ ተስማምቶ መጓዝ አይሆንልንም፡፡ ከረዥም ጊዜ ጀምሮ እንደባህል የተያዘ ፈሊጥ ነው፡፡

አይጥና ድመት የታረቁ ለታ ባለግሮሰሪው/ባለንብረቱ ወዮለት! አይጥና ድመት እንኳ ታርቀው ጠላታቸውን የሚያጠቁበት ቀን ይመጣል ነው የሚሉን፡፡ “የማይለወጥ ነገር የለም – ከለውጥ ህግ በስተቀር” ታሪካችንን ወደኋላ ብንመረምር ምን ያህል እንደተለወጥን ወይም እንደተለዋወጥን መገንዘብ ቀላል ነው፡፡

ስለተሰሩ መንገዶች፣ ስለፈረሱ ቤቶችና ስለተሠሩ ህንፃዎች፣ ስለታሰሩ ሰዎችና ስለተፈቱ ሰዎች፤ ስለተፃፉ ደንቦችና ስለተጣሱ ህጐች፤ ስለማይሸጡ መሬቶችና በሊዝ ስለተወሰዱ መሬቶች፤ ስለማይነኩ ሰዎችና ኋላ ስለተወረወሩ ሰዎች፡፡ ለውጥ አይቀሬ ነው፡፡ ህገመንግስቱን እንኳን “የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል አይደለም ሰው ነው የፈጠረው ሰው ይለውጠዋል፡፡” ብለው ነበር የቀድሞው መሪ፡፡ የብሔር ብሔረሰብ አካሄዳችንም ወደ ኢንዱስትሪ ልማት የሚሸጋገርበት ቀን ሊመጣ ይችላል፡፡

“ዘለዓለም ውሻ ሆኖ ከመኖር አንድ ቀን አንበሳ ሆኖ መሞት” የሚለውን መዘንጋትም ተገቢ አይሆንም፡፡ ሁሉም ወቅት ወቅት አለውና! ሁኔታዎችን እንደየአመጣጣቸው መመዘን፣ እንደየልኬታቸው ዓይነተኛ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ በደስታ ሰዓት ደስታችንን መግለጽ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ የሚያዘናጉንን ሁኔታዎች፤ ይሆነኝ ብሎ ማሰብ ወሳኝ ነው! ይሄ በፖለቲካም፣ በኢኮኖሚም፣ በባህልም፣ በሥነ አዕምሮአዊ ሂደትም፤ ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ መንግሥትም፣ ፓርቲም፣ ግለሰብም ተሁኖ ቢታሰብ፤ ዋናው ነገር ይሄው ነው፡፡

የአባይ ጉዳይ ላይ ያጠላበት የፖለቲካ ድባብ አሁን ሊገፈፍ ይገባል!! ግርማ ሠይፉ ማሩ

የውሃ፣ ኢነርጂና መስኖ ሚኒስትር በአባይ ተፋሰሰ ሀገሮች መካከል በተለይም በግብፅ፣ በሱዳን እና ኢትዮጵያ መካከል ሲደረግ የነበረውን ውይይት እንዲሁም የህዳሴ ግድብ ያለበትን ደረጃ አሰመልክቶ ለምክር ቤት አባላት በባለሞያ የታገዘ ገለፀ ለማድግ ህዳር 22/2006 በምክር ቤቱ ተገኝተው ነበር፡፡ ይህ ገለፃ እና ማብራሪያ ከዚህ ቀደም ለዩኒቨርስቲ ማህበረሰብ ቀርቦ የነበረ መሆኑ በሚዲያ ተከታትለናል፡፡ በእኔ እምነት ቀድሞ መቅረብ የነበረበት ለምክር ቤቱ ሆኖ ከዚያ ቀጥሎ በየደረጃው ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ቢቀርብጥሩ የፕሮቶኮል አካሄድ ነው ለማለት እችል ነበር፡፡ ለማነኛውም ፕሮቶኮሉን እነተው እና በዚህ ደረጃ ለህዝብ ለማቅረብ ተነሳሸነቱ መፈጠሩ የዘገየም ቢሆን ተገቢ ነው ብዬ መውሰድ አልቸገርም፡፡ “ዘገዬ” የሚለውን ቃል ኢህአዴግና ሹሞቹ በጓዳ ግምገማ ካልሆነ በአደባባይ ውይየት ጊዜ ደስ አይላቸውም፡፡

በነገራችን ላይ ይህ ማብራሪያ አሁን መቅረቡ ጥሩ መሆኑን፤ ነገር ግን ዘግይቷል በሚል ለውሃ፣ መሰኖ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ለሰጠሁት አስተያየት ሚኒስትሩ “አልዘገየም ድርድሩ እዚህ ጋ የደረሰው በጥቅምት ወር ነው፡፡” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በእኔ እምነት ኢትዮጵያዊያን ማወቅ ያለባቸው የሶስትዮሽ ድርድሩን ሳይሆን አጠቃላይ መንግሰት ግድቡን ለመገንባት የሄደበትን መንገድ ነው፡፡ በተለይ ኢትዮጵያዊ ምሁራን እና ጋዜጠኞች ከግብፅ እና የግብፅ ወዳጆች በተለያየ መልክ በሚያስረጩት መረጃ ሳይሆን በቀጥታ ከሀገራቸው ታማኝ መረጃ አግኝተው ጠንካራ አቋም እንዲይዙ ማድረግ የግድ የሚል ነው፡፡ የምሁራኑ እና የጋዜጠኞች መረጃ ማግኘት ያለጥርጥር ህዝቡ ሀገር በቀል መረጃ እንዲያገኝ ዋናኛ መንገዶች ናቸው፡፡ የዘገየ ማብራሪያ የምለውም ስለግድቡ አጠቃላይ ሁኔታ ነው እንጂ ስለ ሶስትዮሽ ውይይት ሂደትና ውጤት አይደለም፡፡ ለምሳሌ በአባይ ተፋሰስ ላይ ቀደም ሲል በአሜሪካ ድጋፍ ቀጥሎም እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2005/6 በተፋሰስ አገሮች ትብብር ሱዳን እና ግብፅ ጨምሮ በተደረገው ጥናት ሶሰት የግድብ ቦታዎች ተመርጠው የአሁኑ “ቦርደር ሳይት” በመባል የሚታወቀው የግንባታ ቦታ በሁሉም ተመራጭ እንደነበር ብዙ የሚያውቅ ሰው የለም፡፡ በአቶ አለማየሁ ተገኑ አገላለፅ “ፕሮጀክቱ ግማሽ
ድረስ በትብብር የተሰራ ነው”፡፡ ይህን የትብብር ስሜት ያፈረስው ምን አልባትም የግብፅ ከልክ ያለፈ አልጠግብ ባይነት እና በኢትዮጵያ ምድር ላይ የሚገኝ ቢሆንም አባይን የሚመለከት ፕሮጀክት በባለቤትነትን የመያዝ እና የማስተዳደር ፍላጎት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የመጣው ከንቀት ጭምር ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከግብፅ ጋር በሽግግር መንግስት ወቅት የገቡት ቃል ወይም ስምምነት ለመናቃችን አንዱ የቅርብ ምሳሌ ነው፡፡ ኦቶ መለስ ይህን ቃላቸውን አጥፈው፣ ይህ ፕሮጀክት በኢትዮጵያዊያን ቁጥጥር እና ባለቤትነት እንዲካሄድ የወሰዱት አቋም ተገቢም ትክክል ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ተመሳሳይ አቋሞች በብዙ ሁኔታዎች የታዘብን ቢሆንም
በዋነኛነት “ባንዲራ ጨርቅ ነው” በባንዲራ ቀን አከባበር፤ “የአክሱም ሀውልት ለወላይታ ምኑ ነው” በብሔር ብሔረሰቦች በዓል አከባበር ቀጥሎም በብሔር መለያየትን “ልዩነታችን ውበታችን” በሚል መፈክር መታጀቡ እና በሌሎች ሁኔታዎችን የተገነዘብን ሰዎች የሶስት መቶ ስልሳ ዲግሪ መታጠፍ አድርገን ልንወስደው እንችላለን፡፡ ለማንኛውም ኢትዮጵያን እና ህዘቦቿን ወደሚጠቅም አቋም በፈለጉት ዲግሪ መታጠፍ ቢዘገይም በአዎንታ መቀበል ይኖርብናል፡፡

በህዳሴ ግድብ ዙሪያ በሚደረገው የሶስትዮሽ ድርድር ጥሩ አካሄድ ሊባል የሚችለው የውጭ ዜጎችን በመጠቀም ዙሪያ በመንግሰት የተያዘው አቋም ነው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከወንድሞቻችን ኤርትራዊያኖች ጋር በመሪዎች ፍላጎት በገቡት “የድንበር” ተብዬ ግጭት፣ ችግሩን ለመፍታት በተለይም የኢትዮጵያን ጥቅም ለማስጠበቅ የሀገር ውስጥ ባለሞያዎችን እና ታሪክ አዋቂዎቸን ባለመጠቀም የደረሰባትን ኪሳራ በደንብ የተረዱት ይመስላሉ፡፡ በአባይ ጉዳይ ዋናዎቹ ተዋናዮች ኢትዮጵያዊያኖች እንደ ነበሩ ለመረዳት ችለናል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም በቀጣይ ይህን ጉዳይ አስመልክቶ በሚደረግ ውይይት ከውጭ የሚባል አይኖርም፤ የሚያስፈልግ ባለሞያ ቢኖር ቀጥረን አገልግሎት ከመስጠት በዘለለ ገብቶ መፍተፈት አይፈቀድም፡፡ የሚል አቋም ኢትዮጵያ ይዛለች የሚለው መስመር እሰይ የሚያስብል ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት አቋም የሚመራው በኢህአዴግም ቢሆን መደግፍ የግድ ይለናል፡፡

በዚህ አጋጣሚ እሰከ ዛሬ በነበረው ውይይት ከውጭ ሀገር ማለትም ከጀርመን፣ ከእንግሊዝ፣ ከፈረንሳይ እና ከደቡብ አፍሪካ ተወክለው ምክረ ሃሳብ ያቀረቡት ባለሞያዎች ጥንቅር “ለምን ከወዳጆቻችን ከነቻይና አልመጣም?” የሚል ፈገግ የሚያሰኝ በዚያውም የህውሃት አባላት አሁንም መንግሰት ሶሻሊሲት እንደሆነ የሚያሳብቅ ጥያቄ አንድ የምክር ቤት አባል ሰንዝረዋል፡፡ በዚህ ጉዳይ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምንከተለው ይበሉ እንጂ አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ በዚህ የሚስማሙ እንዳልሆነ በተለያየ መግለጫ ታዝበናል፡፡ እኛም ብንሆንን የምንስማማው አቶ ሀይለማሪያም ደሳለኝ በሚገልፁት መስመር ነው፡፡ የኢህአዴግ አብዮታዊ ዲሞክራሲ ከካፒታሊዝም ሳይሆን ወደ ሶሻሊዝም የሚጠጋ ርዕዮት እንደሆነ ነው የሚገባን፡፡ መድበለ ፓርቲ ስርዓት፣ ነፃ ገበያ፣ የግል ሀብት፣ ወዘተ ለእርዳታ ሰጪዎች ሲባል የሚቀርቡ ሹፈቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ሹፈቶች ግን ይዋል ይደር አንጂ ዋጋ የሚያስከፍሉ ናቸው፡፡

በግሌ የኢህአዴግ በደል ከፍቶ ፅዋው ሞልቶ ቢፈስ እንኳን የሀገሬን ጥቅም አሳልፌ የምሰጥበት ምንዳም ሆነ የግፍ መጠን እንደሌለ በተደጋጋሚ ይፋ አድርጊያለሁ፣ ከዚህ የግል እምነቴ ጋር የሚፃረር ፓርቲም ሆነ ሌላ ስብስብ ጋር እንደማልሰራ አውቃለሁ፡፡ እንደዚያም ሆኖ የመንግሰት ሹማምንት የአባይ ግድብን ያህል ትልቅ ፕሮጀክት ይዘው ተቃዋሚና ገዢ ፓርቲ የሚል ክፍተት መፍጠር እንደሌለባቸው ሲነገራቸው፣ በተግባር የሚሰሩትን ሀቅ ወደ ጎን ትተው ጉዳዩን በሙሉ ፕሮፓጋንዳ ያደርጉታል፡፡ ኢህአዴግ ለፕሮፓጋንዳ የሚከፍለው መሰዋዕትነት የፈለገ ውድ ቢሆን ለመክፈል ዝግጁ ነው፡፡ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ስለግድቡ በቂ መረጃ በሌላቸው እና ይልቁንም ግርማ ሠይፉ ማሩ በመንግሰት የሰብዓዊ መብት አያያዝ ፍፁም ደስተኛ ባልሆኑበት ሁኔታ፤ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን መንግሰትን ደግፈው ገንዘባቸውንያለምንም ጥያቄ እንዲቸሩ ይጠይቃል፡፡ በሀገር ውስጥም ቢሆን ሁሉን ተዉት ገንዘብ አምጡ ዘመቻ የሚያስገርም ነው፡፡ በውጭ የሚኖሩኢትዮጵያዊያን ይህን ግድብ በሚያስደንቅ ሁኔታ ሊገነቡት የሚችሉበት አቅም እንዳለ ተገንዝቦ ግብፅን አንገት የሚያስደፋ መንገድ ከመቀየስ ይልቅ አሁንም በውጭ የሚገኙትን ዜጎች መከፋፈል ተገቢ አይደለም የሚል እምነት አለኝ፡፡ መንግሰት ከዚህ አንፃር
የሚጠበቅበት ለውጥ፤ ግብፅን አና ወዳጆቿን እሞኑኝ ብሎ ለልምምጥ ከሚያጠፋው ጉልበትና ሀብት የሚበልጥ አይደለም፡፡ መንግሰት ከዚህ አንፃር የሚከተለውን የኮሚኒኬሽን ስትራቴጂ እንደገና መገምገም እና ሁሉንም በሚያሳትፍ መልኩ መቀረፅ እንዳለበት ማስገንዘብ ቢዘገየም የረፈደ አይደለም፡፡ ኢህአዴግ ግን የሚሰማ አይመስልም፡፡ ማን ነው ኢህአዴግ ሀፍ እንጂ ጆሮ የለውም ያለው?

በአባይ ዙሪያ በኢየትዮጵያ ለሚታሰብ ማንኛውም እንቅስቃሴ በቂ ተቃውሞ በግብፅ ስለ አለ በሀገር ውስጥ ሌላ ጠላት ለምን ትፈልጋላችሁ? ለሚል ጥያቄ ኢህአዴግ ሆደ ሰፊ መሆን አይችልም፡፡ ኢህአዴግ በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ገንዘብ ማግኘት የሚፈልገው፣ ለአብታዊ ዲሞክራሲ እግረ መንገዳቸውን ገብረው እንዲሆን ይፈልጋል፡፡ እኔ እንደ ተቃዋሚ ፓርቲ አባል ለስልጣን ነው ትግል የማደርገው፡፡ ስልጣን ብንይዝ ይህች ሀገር ኢነርጂ እንደሚያስፈለጋት ለማወቅ ስልጣን መያዝ የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ የአባይን ግድብ ለመገንባት መንግሰት የሚያወጣውን ዕቅድ በተመለከተ የተሟላ መረጃ እንዲኖረኝ የግድ ይላል፡፡

የኢትዮጵያ ሚዲያዎች ከዚህ አንፃር በጭፍን የአባይን ግድብ እንዲደግፉ እንጂ መረጃን መሰረት አድርገው ትንተና እንዲሰሩ እና የራሳቸውን ምክረ ሃሳብ እንዲሰጡ እድል የላቸውም፡፡ ለዚህ ጉዳይ የሚፈለጉት ልማታዊ የሚባሉት ጋዜጠኞች ብቻ ናቸው እነርሱም መንግሰት የሚለውን እንደ በቀቀን መድገም ነው የሚጠበቅባቸው፡፡ በግብፅ ግን የግልም ሆነ የመንግሰት ሚዲያዎች ለሀገራቸው ይጠቅማል ያሉትን እንዲዘግቡ መረጃ ይስጣቸዋል፡፡ ማግለል ይቅር ስንል የፖለቲካ ፓርቲዎችን እና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንን
ወይም ትውልደ ኢትዮጵያዊያንን ብቻ ሳይሆን ሚዲያውንም ጭምር ነው፡፡ አሁንም የአባይ ጉዳይ እና መረጃ ሁሉም ሚዲያዎች በሚያሳትፍ መልኩ ለሚዲያዎች መሰጠት ይኖርበታል፣ ሚዲያዎችም ይህን ኃላፊነት እንደሚወጡ ጥርጥር የለኝም፡፡ ለዚህም ማሳያ የ “ፋክት” አምደኞች ቤተሰብ የነበረችው መፅሄት አዲስ ታይምስ ከዓመት በፊት የአባይን ጉዳይ በልዩ ዕትም ቅፅ 1 ቁጥር 9 ህዳር 2005 ማውጣቷ እና በዚህ ዕትም ያስተላለፈችው መልዕክት ድጋሜ መነበብ የሚገባው ነው፡፡

በዚህ አጋጣሚ በኤክሰፐርቶች ፓናል ውስጥ ተሳታፊ ለሆናችሁ ኢትዮጵያዊያን ወገኖች ሁሉ ከመቀመጫዬ ብድግ ብዬ አድናቆቴን መግለፅ እፈልጋለሁ፡፡

ግብፆች የአባይ ጉዳይ ሲነሳ የፖለቲካ ልዩነታቸውን ትተው እንደ ግብፅ ሲያስቡ እኛን መለያየት ለምን ያስፈልጋል? የአባይ ግድብ ፕሮጀክት በተግባር የኢትዮጵያ ህዝብ ፕሮጅክት አንዲሆን የፖለቲካ ድባቡ ላይ ያጠላው የፕሮፓጋንዳ አዚም ሊገፈፍ ይገባል፡፡ አንድነት ፓርቲ ኢትዮጵያ የአባይ ወንዝን መጠቀም ተፍጥሯዊ መብቷ ነው ይላል፡፡ ይህ የማይገሰስ መብት ላይ ምን ፕሮፓጋንዳ ያስፈልጋል፡፡ የዛሬው መልዕክቴ ዋና ማጠንጠኛ በሀገር ጉዳይ እንዳንግባባ አዚም ያደረገብን ማን ነው? የዚህ አዚም መፍቻ ቁልፍ መተማመን እና ሀገራዊ ዕርቅ ይመስለኛል፡፡
መልካም በዓል ቸር ይግጠመን !!!!!!

[email protected]

‹‹የሕዝብ መብት ከሚቃወም የፖለቲካ ድርጅት ጋር መሥራት አስቸጋሪ ነው›› ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ
‹‹የአንድነትን አቋም ሳያውቁ የፓርቲው አባል ሆነዋል ለማለት ያስቸግራል›› m አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ

ላለፉት ሁለት ዓመታት የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) ሊቀመንበር የነበሩትና ለ45 ዓመታት በፖለቲካ ውስጥ እንደቆዩ የሚናገሩት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ከጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም.
ጀምሮ ከማንኛውም ዓይነት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታወቁ፡፡ በአሁኑ ወቅት ከፖለቲካው ዓለም ለመሰናበት የወሰኑት አንድነት ፓርቲ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ ስላልተመቻቸው ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ጥያቄ ቢያቀርቡም፣ ምላሽ ባለማግኘታቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ እንደገለጹት፣ መድረክ ግንባር ከመሆኑ አስቀድሞ ባነሳቸው ሐሳቦች ላይ ሁሉም ድርጅቶች ጠቅላላ ጉባዔ በማድረግ ከተወያዩባቸው በኋላ ስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡ መስማማታቸውንም ለመድረክ በመግለጽ መድረክ ወደ ግንባር መሸጋገሩን አስታውሰዋል፡፡

በሚያዝያ ወር 2005 ዓ.ም. በአንድነት ፓርቲና በእሳቸው የአመለካከት፣ የአቋምና የአቅጣጫ ልዩነት መፈጠሩን የገለጹት ዶ/ር ነጋሶ፣ አንድነት ፓርቲ መድረክ ወደ ግንባር የተቀየረው በጠቅላላ ጉባዔውና በብሔራዊ ምክር ቤቱ እምነትና ውሳኔ ሳይሆን በአመራሮች መሆኑን በመጥቀስ፣ እንደማይስማማ በዚያን ወቅት ባደረገው ግምግማ ላይ በመግለጹ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

መድረክ ወደ ግንባር ከመቀየሩ አስቀድሞ ይፋ ባደረገው ፕሮግራም ላይ ሁሉም የፖለቲካ ድርጅቶች ተወያይተውና ተመካክረው በሕገ መንግሥት ጉዳይ፣ በቤት ጥያቄና በሌሎችም በተነሱ ነጥቦች ላይ መስማማታቸውን የጠቆሙት ዶ/ር ነጋሶ፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 39 ላይ ብቻ ልዩነት እንዳለው አንድነት ገልጾ የሽግግር ሒደቱ በሰላም መፈጸሙን አስታውሰዋል፡፡

ሽግግሩ ወራትን ካስቆጠረ በኋላ በሕገወጥ መንገድ እንደተደረገ በማስመሰል ወደኋላ መመለስ አሳፋሪ ድርጊት ከመሆኑም በተጨማሪ የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤትና የፓርቲው የሕዝብ ግንኙነት፣ ፓርቲው የማይስማማበትን ነጥብ ይዞ ወደ መድረክ በመሄድ መወያየት ሲገባቸው፣ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ መስጠታቸው ትክክል አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም የነበሩትን የተሳሳቱ ሒደቶች በመጥቀስ እርማት እንዲደረግ ዶ/ር ነጋሶ ለአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ሰብሳቢ የተለያዩ ጥያቄዎችን ያቀረቡ ቢሆንም፣ ምላሽ ሊያገኙ አለመቻላቸውን ተናግረዋል፡፡

ሌላው ዶ/ር ነጋሶ የሚያነሱት ጥያቄ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 39 ላይ የተጠቀሰውን ‹‹የብሔር ብሔረሰቦች መብት የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን እስከ መገንጠል›› የሚለውን የሕዝቦች የመብት ጥያቄ አንድነት ውድቅ ማድረጉ ተገቢ አለመሆኑን ሲሆን፣ ‹‹የሕዝብን መብት ከሚቃወም የፖለቲካ ድርጅት ጋር መሥራት አስቸጋሪ ነው፤›› ብለዋል፡፡

አንድነት የመድረክን ወደ ግንባር መቀየር የማይቀበለው ‹‹የውህደት›› ኅብረ ብሔራዊ ፓርቲ መመሥረት እንዳለበት ስለሚፈልግ መሆኑን የጠቆሙት ዶ/ር ነጋሶ፣ በሕጋዊና በትክክለኛ መንገድ ስምምነት የተፈጸመበትን ‹‹ግንባር›› ‹‹ውህደት›› ካልሆነ ማለት የማይሆንና የማያስኬድ መንገድ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ያልተስማሙባቸውን ነጥቦችና ስምምነት ከተደረገ በኋላ ወደ ኋላ መመለስ አግባብ አለመሆኑን በመጠቆም ላቀረቧቸው ጥያቄዎች የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ምላሽ በመንፈጉ ምክንያት፣ ዶ/ር ነጋሶ ከፖለቲካው ዓለም መሰናበታቸውን ይፋ ቢያደርጉም፣ ቀደም ብሎም ከፖለቲካ ሥራና ተሳትፎ ለመልቀቅ በማኮብኮብ ላይ እንደነበሩ አልሸሸጉም፡፡

ምክንያታቸውንም ሲገልጹ ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም 70 ዓመት ሞልቷቸዋል፡፡ ከዕድሜያቸው ከግማሽ በላይ ለ45 ዓመታት በፖለቲካ ውስጥ ቆይተዋል፡፡ የኦሮሞ ሕዝብን የፖለቲካ ባህል ሲያስታውሱ፣ በኦሮሞ ገዳ ዲሞክራሲ አንድ መሪ ዕድሜው 48 ሲሆነው የአመራር ሥልጣኑን ለወጣቱ መልቀቅ እንዳለበት የሚገልጸውን ተግባራዊ ማድረግ ተገቢ መሆኑንም ማሰባቸውን አብራርተዋል፡፡

ሙሉ በሙሉ ከፖለቲካ ዓለም ራሳቸውን ማግለላቸውን ከዚህ በኋላ በማንኛውም መንገድ ማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ በአባልነትም ሆነ በመአራርነት እንደማይሳተፉ ያረጋገጡት ዶ/ር ነጋሶ፣ ‹‹ጆሮዬ ለፖለቲካ ክፍት ይሆናል፤ የማስበውን በጽሑፍና በአፌ እናገራለሁ፤ አንድነትንም ሆነ ሌሎችንም በመዋቅራዊ መልክ ሳይሆን እደግፋለሁ፤ ሲያስፈልግ እተቻለሁ፤ ሲያስፈልግ እቃወማለሁ፤›› ብለዋል፡፡

አንድነት ፓርቲ ለዶ/ር ነጋሶ ከፖለቲካ መገለል ምክንያት ስለመሆኑ ለተነሳለት ጥያቄ በሕዝብ ግንኙነት አማካይነት ምላሽ ሰጥቷል፡፡

ፓርቲው በቅርቡ አዲስ አመራር መምረጡንና ቀደም ሲል በሊቀመንበርነት ሲመሩ የነበሩት ዶ/ር ነጋሶ፣ ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ የሥልጣን ሽግግሩን ፈጽመው ለብሔራዊ ምክር ቤቱ አቅርበው ሽግግሩን ማፅደቃቸውን የገለጹት የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው ናቸው፡፡

ለብሔራዊ ምክር ቤቱ የአዲሱን አመራር ቀጣይ የሥራ የሽግግር ጊዜ ሲያቀርቡ፣ ከዕድሜያቸው ጋር በተገናኘ ለቤተሰቦቻቸው ራሳቸውን ከፖለቲካ እንደሚያገሉ ቃል መግባታቸውን የተናገሩት አቶ ሀብታሙ፣ በመድረክ ላይ ያላቸውን አቋምም ግልጽ ማድረጋቸውን አክለዋል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ አንድነት መድረክን መገምገሙና ማጥናቱ ትክክልና ተገቢም ነው፡፡ የግንባሩ አባል የሆነ ድርጅት ፖለቲካውን አግባብ ባለው መንገድ እየመራ ነው? አይደለም? የሚለውን ጥናት ማድረግ ተገቢ ነው ካሉ በኋላ፣ መድረክ አሁን ባለው ሁኔታ የሚታየውን ነገር ሁሉ ማሻሻያ በማድረግ ሊቀጥል ይገባል የሚል አቋም እንዳላቸው መናገራቸውን አቶ ሀብታሙ ገልጸዋል፡፡

አንድነት ፓርቲ መድረክ ወደ ውህደት በማደግ አንድ ግዙፍ ብሔራዊ ፓርቲ እንዲፈጠር ያቀረበውን ሐሳብ በቀላሉ ሊሳካ የሚችል ባለመሆኑ፣ ሐሳቡን እንደማይደግፉም ዶ/ር ነጋሶ ማሳወቃቸውን አቶ ሀብታሙ ጠቁመዋል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ ያነሱትን የልዩነትና የድጋፍ ሐሳብ አንድነት ፓርቲ እንደሚያከብር የገለጹት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው፣ ፓርቲው ግን ግልጽ የሆኑ የፖለቲካ አማራጮች እንዳሉት፣ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ትግልን ወደፊት ለመግፋት ብሔራዊ ምክር ቤቱና ጠቅላላ ጉባዔው አስቀድሞ ባዘጋጁዋቸውና በሚያሻሽሉዋቸው ነጥቦች ትግሉን እንደሚቀጥል አስረድተዋል፡፡

አንቀጽ 39ን በሚመለከት አንድነት የብሔር ብሔረሰቦችን መብት በተመለከተ ሕገ መንግሥቱ የሚያነሳቸውን ነጥቦች ፍፁም በሆነ ሁኔታ እንደሚያከብር የተናገሩት አቶ ሀብታሙ፣ ዶ/ር ነጋሶ የአንድነት ፓርቲን አቋም በግልጽ ሳያውቁ የፓርቲው አባል ሆነዋል ለማለት እንደሚያስቸግር አክለዋል፡፡ አንድነት ፓርቲ ከአንቀጽ 39 የማይቀበለው በመጨረሻው ንዑስ አንቀጽ ላይ የተቀመጠውን ‹‹እስከ መገንጠል›› የሚለውን ሐረግ መሆኑን ይህንንም በኢትዮጵያ ሉዓላዊነትና አንድነት ላይ የተቃጣ አደጋ በመሆኑ፣ መቼም ቢሆን የአገሪቱን ሉዓላዊነትና አንድነት ለማንም ለድርድር እንደማያቀርብ በግልጽ ሊታወቅ እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ ላለፉት 45 ዓመታት በቆዩበት የፖለቲካ ሕይወታቸው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባል፣ እንዲሁም የኢሕአዴግ አባል የሆነው የኦሮሞ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) አመራር እንደነበሩ አይዘነጋም፡፡ ከኢሕአዴግ ጋር ከመለያየታቸው በፊት ለስድስት ዓመታት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በመሆን አገልግለዋል፡፡ ከዚያም ከቀድሞ የአገር መከላከያ ሚኒስትር አቶ ስዬ አብርሃ ጋር በመሆን የአንድነት ፓርቲ አባል ከመሆናቸውም በላይ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ የፓርቲው አመራር አባልና ሊቀመንበር መሆን ችለው ነበር፡፡