(ተረፈ ወርቁ):- “… እንደው እነዚህ በአሜሪካ የሚገኙት አባቶች እንደምንም ብለው ተጠናክረው በአገራችን በኢትዮጵያ በእነርሱ በሚመራው በአሜሪካው “ሲኖዶስ” ሥር ያለ/የሚመራ አንድ እንኳን ቤተ ክርስቲያን መመሥረት ቢችሉ በየቦታው ተበታትኖ ያለውን የተሃድሶ እንቅስቃሴ አንድ ማድረግ መምራት ይቻል ነበር እኮ …።”

ይህ ቁጭት፣ ምሬት አዘል ቃል በአንድ  ወቅት የኢትዮጵያን ቤ/ን እናድሳለን ብለው ከተነሡ ሰዎች መካከል ማህበር አቋቁሞና ከአንዳንድ ስለ ሃይማኖታቸው በቂ የሆነ መሠረት ከሌላቸውና የእውነት ዕውቀትን በፍቅር ካልተቀበሉና እንደ “ዘመነ መሳፍንቱ” – የባላባቶች ዘመን “አወዳሽና አንጋሽ” ፈላጊ በሆኑ ባለ ጠጋዎች፣ ወይዛዝርት፣ ነጋዴዎች ምጽዋትና እንዲሁም ከውጭ አገር በሚላክለት ዶላር (በተለይ ከዱባይና ከአሜሪካ) በዐሥር ሺዎች የሚገመት ዘመናዊ ቤት/አዳራሽ ተከራይቶ የተሐድሶን እንቅስቃሴ ለማስፋፋት ላለፉት 20 ዓመታት እየደከመ ያለ ሰው የተናገረው ምሬት ያዘለ ቃል ነው። ለነገሩ ይህ ማህበር በነጋ ጠባ ራሳቸውን በሾሙ በጎበዝ አለቆች የሥልጣን ይገባኛልና በጥቅም ግጭት ሲፈርስ ሲሠራ የኖረ፣ እንዳሰቡትና እንዳለሙት እንኳን የኢትዮጵያን ቤ/ን ሊወርሱ ቀርቶ የሕልም ዳቦቸውን እየገመጡ በቀቢፀ ተስፋ ተውጠው ነው ያሉት።

ይህን የተሐድሶ አራማጆች፣ “ተጠሪነቱ  ለአሜሪካው “ሲኖዶስ” የሆነ ቤ/ን በአገር ቤት ቢያቋቁሙ” የሚለው የጥፋት፣ የክፋት ሐሳብ/የሕልም ዓለም ምኞታቸውን ያነሳሁት አለምክንያት አይደለም። በአሜሪካ የሚገኙት ራሳቸውን “ሕጋዊው የኢትዮጵያ ቤ/ን “ሲኖዶስ”/ስደተኛው “ሲኖዶስ” በሚል የሚጠሩ አንዳንድ አባቶችና አገልጋዮች በቤተ ክርስቲያኒቱ ዶግማና ቀኖና ያላቸው የተዛባ ምልከታ፣ አፍቃሪ-ፕሮቴንስታዊ/Pro-Protestant አስተምህሮአቸው የተነሳ የተሃድሶ አራማጅ ነን ከሚሉ ሰዎች ጋር “የጡት ልጅን” ያህል በጥብቅ ተዛምደዋል፤ ተጣብተዋል። ይህ ደግሞ አለምክንያት የሆነ አይደለም።

እስቲ እነዚህ የተሃድሶ አራማጅ ነን ባዮችን ዓይናቸውን ወደ ምዕራቡ ዓለም/አሜሪካ እንዲያነሡ ያደረጋቸውንና በአሜሪካ ያለው “ሲኖዶስ”ም – “እልል በቅምጤ” እንዲሉ እነዚህን ሰዎች በደስታ እጃቸውን ዘርግተው እንዲቀበሉ ያደረጋቸውን ምክንያቶቹን በጣም በጥቂቱ ለማየት እንሞክር።

ለረጅም ዓመታት በኖሩበት የምዕራቡ ዓለም የዘቀጠ ባህል ተፅዕኖ ስር የወደቁ የአሜሪካው ስደተኛ “ሲኖዶስ” አንዳንድ “Liberal” ነን ባይ አባቶችና አገልጋዮች በፕሮቴስንታታዊ አስተምህሮአቸውና ሥርዓት አልበኝነታቸው በአገር ቤት የተለዩ ሰዎች መጠለያና መሸሸጊያ መሆናቸው ነገር መቼም ፀሐይ የሞቀው የአደባባይ ምስጢር ነው።

“ወንድሜን ሥጋ መብላት የሚያሰናክለው ከሆነ ለዘላለሙ ሥጋን አልበላ።” የሚሉ ቅዱሳን አባቶችና ሐዋርያት ባለፉባት ቤ/ን ስለ “አሳማ ሥጋ” እና ስለ “ኦርጋን መሳሪያ” ክርክር እያስነሡ ምእመናንን የሚያለያዩ ትምህርትን የሚያስተምሩ አባቶችንና አገልጋዮችን የታዘብነው በዚሁ በአሜሪካው “ሲኖዶስ” ነው።

ቁሳዊነት/Materialism፣ ደስታን የማሳደድ የሕይወት ዘይቤ/Hedonism፣ ግላዊነት/Individualism፣ ዘመናዊነት/Modernism …ወዘተ በገነነበት ዓለም የሚኖሩ እነዚህ አንዳንድ አባቶችና አገልጋዮች በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ መንገድ የምዕራቡን ዓለም መንፈሳዊ ተቋማት ከመገዳደር አልፈው እያፈራረሷቸው የሚገኙትን እነዚህን ዓለማዊ የሆኑ አስተሳሰቦችንና የኑሮ ዜይቤዎችን በዘመናዊነት ካባ ወደ ቤ/ን ለማስገባት እየተጣጣሩ ነው።

በዛን ሰሞን በአሜሪካው “ሲኖዶስ” የሚገኙ አባቶችና አገልጋዮች፣ “በኦርጋን መዘመር አለበት!” በሚል መግለጫ እስከማውጣት የዘለቁበት አካሔዳቸው – የአገራቸው/የማንነታቸው መግለጫ፣ የባህል መሳሪያዎቻችን ከሆኑት ከእነ በገና፣ ማሲንቆ፣ ክራር፣ እምቢልታና መለከት …ወዘተ ተለያይተው ምን ያህል በምዕራቡ ዓለም ባህል ተጠልፈውና ተጠላልፈው እንደወደቁ አንድ ትልቅ ማሳያ ነው።

እነዚህ ሰዎች አውቀውትም ሆነ ሳያውቁት ለሺ ዘመናት የትናንትና  ታሪካችን፣ የሥልጣኔያችንና የማንነታችን መገለጫና መታወቂያ ከሆነና የቅዱስ ወንጌል መሠረት ካለው ክርስቲያናዊ ባህላችንና ትውፊታችን፣ ወግና ሥርዓታችን ትውልዱን በማናወጥ የማንነት ቀውስ/Identity Crisis ውስጥ እንዲገባ የማድረግ ዘመቻ ውስጥ እየተዘፈቁ ነው።

ሌላኛዉ ምክንያት የአሜሪካው ሲኖዶስ የአባላቱን ቁጥር ከፍ በማድረግ ሀያልነቱን ለማሳየት ሲባል ወደ እነርሱ የሚመጡትን ሰዎች/አገልጋዮች ብዙም ጥያቄ ሳያበዙ ነው የሚቀበሏቸው። ለነገሩ ይህን ለማድረግም ጠንካራ የሆነ እንደ ሊቃውንት ጉባኤ ያለ መንፈሳዊ ተቋም አለመኖሩም ሌላኛው ጉዳት ነው። ስለዚህም ይህ ጥብቅነት የሌለው ብዛትን እንጂ ጥራትን ከቁጥር ውስጥ ያልሰገባው አሠራር አንዳንዶችን የራሳቸውን አስተምህሮ እንደፈለጋቸው ለመዝራት እንዲችሉ አስችሎአቸዋል።

እዚህ ጋር አባላትን ከማብዛት አንፃር በደቡብ አፍሪካ የሆነ አንድ ታሪክ ላንሳ። እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ቤ/ን በጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን ሕዝቦች የነፃነት ተጋድሎ ታሪክ ውስጥ ያላት ስም ትልቅና የከበረ ነው። ደቡብ አፍሪካውያን ለኢትዮጵያ ቤ/ን ያላቸው ይህ ፍቅርና ክብር ከመቶ በላይ ዓመት ያስቆጠረው ለነፃነት ያበቃቸው ANC ፓርቲያቸው የተመሠረተው ቄስ ጆን ዱቤ በተባሉ የቤተ ክርስቲያናችን አባልና ተከታዮቻቸው ነው።

ይህ ታሪክ እውነታ የኢትዮጵያን ቤ/ን በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ጠንካራ መሠረት እንዲኖራት አድርጓል። እናም ቤተ ክርስቲያናችን በደቡብ አፍሪካ ምድር ከአምስት የሚልቁ ቤ/ን፣ በማህሌታዊው ቅዱስ ያሬድ ስም የተመሰረተ አንድ ገዳምና ከሃያ በላይ መንፈሳዊ ጉባኤያት አሉ። ታዲያ ከእነዚህ ጉባኤያት መካከል ማፊኬኔ በተባለ ከተማ ያለ አንድ ጉባኤ በወያኔ በሚመራ ሲኖዶስ እንዴት ትመራላችሁ በሚል የፖለቲከኞች ስብከት፣ መንፈሳዊ፣ አስተዳደራዊ ጥያቄና ብሶት ምክንያት ራሳቸውን ለይተው ግንኙነታቸውን በአሜሪካው ሲኖዶስ ስር በሚመራው ቤ/ን ስር ሆነው ነበር።

ይሁን እንጂ በአሜሪካው ሲኖዶስ ስር ያሉ አባቶችና አገልጋዮች መንፈሳዊ አገልግሎታቸው በዋና ከተማው በጆሃንስበርግ፣ በፕሪቶሪያና በአካባቢው ብቻ የተወሰነ በመሆኑ እነዚህ ከጆሃንስበርግ በብዙ ኪሎ ሜትር ርቀው የሚገኙት የማፊኬኔ ጉባኤ የ”እኛ አባል ናቸው” ከሚል ንግግር ባለፈ ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎትና አስተዳደራዊ መመሪያ ለመስጠት የሚችሉበት ሁኔታ ላይ አልነበሩም። በሂደትም የጉባኤው አባላት እንዳሰቡት መንፈሳዊ አገልግሎት ባለማግኘታቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያ ቤ/ን በደቡብ አፍሪካውያን መካከል እየተስፋፋች መምጣቷ ያሳደረባቸው ባይተዋርነት የተነሳ በመጨረሻ ይቅርታ ጠይቀው ወደ ኢትዮጵያ ቤ/ን የተመለሱበትን ታሪክ አስታውሳለሁ።

በመጨረሻም ለማንሳት የምፈልገው ምክንያት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ አስተዳደር ውስጥ እጃቸውን የሚያስረዝሙ ፖለቲከኞቻችን የፈጠሩት ክፍተት፣ በዘመነ ኢሕአዴግ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር ባሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች መካከል የተለያዩበትን አሳዛኝ የታሪክ አጋጣሚ ለመጋፈጥ ተገደናል።  ከዚሁ ጋር ተያይዞም  ለአብነትም በአሜሪካ በስደት ላይ የሚገኙ አባቶቻችን በግንቦቱ ሲኖዶስ ስብሰባቸው ያወጡትን ባለ 15 ነጥብ የአቋም መግለጫ መመልከት በቂ ነው። የቤተ ክርስቲያን ሳይሆን የአንድ የመንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲ ያወጣው ሊያውም ስሜት አልባና አደናጋሪ የአቋም መግለጫ ነው የሚመስለው።

ሌላው በጣሙን የገረመኝ ነገር ደግሞ የአሜሪካው ሲኖዶስ በዚሁ መግለጫቸው ከወያኔ መንግሥት ጋር ተባብሮ የሚሠሩትንም ሰዎችን ሁሉ አውገዘናል የሚለው ዐርፍተ ነገር ደግሞ ይበልጥኑ አስገረመኝ፣ አሳዘነኝም። ይሄ ማውገዝ፣ መወጋገዝ በቃ ባህል ሆነ ማለት ነው?!

ከጥቂት ዓመታት በፊትም የአሜሪካው ሲኖዶስ አንድ ሊቀ ጳጳስ የሆኑ አባት፣ “በወንጌል እመኑ፣ ንስሓ ግቡ።” ከሚለው እጅግ በከከበረው የዐዲስ ኪዳን የጌታችንና የመድሀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል አገልግሎት ወርደው፣ “በኢትዮጵያ አየር መንገድ እንዳትጓዙ፣ የወያኔ ሽርኮች የሚያስመጡትን በርበሬና ሽሮ እንዳትገዙ … ወዘተ በማለት በየቦታው ሲቀሰቅሱ ብናያቸው በጣሙን አፈርንም፣ ተሳቀቅንም።

የባለፈው ሰሞንም በአሜሪካ ያሉ አባቶች በኦርጋን ይዘመር ዘመቻም የዚህችን ጥንታዊት፣ ባለ ታላቅ ታሪክና የገናና ሥልጣኔ ባለቤት የሆነች የአገራችንና የቤተ ክርስቲያናችንን ታሪክና ቅርስ፣ ማንነትና ባህል፣ ሥርዓትና ትውፊት ለማጥፋት፣ ለመናድ ከሚደረግና እንዲሁም በዘመናዊነትና በሥልጣኔ ስም የምዕራቡን ዓለም ባህል ለመጫን/ለማራገፍ ከሚደረግ እኩይ ዘመቻ/ሴራ ተለይቶ የሚታይ እንዳልሆነ ነው የታዘብኩት።

ወደ ሲኖዶሱ መግለጫ ስመለስም በእውነት ያሳፍራል፣ ያሳቅቃልም። ይህ መግለጫ የጥላቻና የፅንፈኝነት መንፈስ ከሚነዳቸው፣ ዕድሜ ዘመናቸውን ከደምና ከቂም በቀል ትርክት መውጣት ካልቻሉት የ60ዎቹ ትውልድ የፓርቲ ስብስብ ማብቂያ የሌለው፣ የነጋ ጠባ የፖለቲካ መግለጫቸው እምብዛም የተለየ ሆኖ አላገኘሁትም።

ለመሆኑ የተሸከምነው ወንጌል የፍቅር፣ የሰላም መልዕክት እንጂ የጥላቻና የመለያየት ወንጌል ነው እንዴ …?! ሌላው የሲኖዶሱ መግለጫ ከበርካታ የፊደል ግድፈቶቹ፣ እዚህም እዛም የተደነገሩት ትርጉም የለሽ ቃላቶች በላይ ደግሞ የቤተ ክርስቲያናችንን/የግእዙን ቋንቋ አጻጻፍ ሥርዓት የተከተለ አይደለም። ለአብነትም በሐመሩ “ሐ” መጻፍ ያለበት በሀሌታው “ሀ” ተጽፏል፣ ለአልፋው “አ” መጻፍ ያለበት በዓይኑ “ዐ”፣ ሌላም ሌላም የማይጠበቁ ስህተቶች ያሉበት መግለጫ ነው።

እንግዲህ በዚህ ሁሉ ውዝግብ ውስጥ – ፖለቲካው፣ ዘረኝነቱ፣ የአስተምህሮ ችግሩ፣ መለያየቱ፣ መከፋፈሉ … ወዘተ ገና ይሄ ነው የሚባል መፍትሔ ሳይበጅለት በአሜሪካ የሚገኙ አባቶች ኤጲስ ቆጶሳት ሹመቱን ተያይዘውታል። ሊያውም ደግሞ በአስተምህሮአቸውና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ጥያቄ የሚነሳባቸውን ሰዎች ሳይቀር ለዚህ ታላቅ ለሆነ መንፈሳዊ ሓላፊነት ሹሞአቸዋል። ይህ ከመንፈሳዊ ቅናት ይልቅ የእልክ የሚመስል የአባቶቻችን ጉዞ ፍጻሜው ምን ሊሆን እንደሚችል የምናየው ነው የሚሆነው።

አንድ ስለምታደርግ ሥጋውና ደሙ እግዚአብሔር በይቅርታው አንድ ያደርገን ዘንድ ሰላምን እንማልዳለን።
እስከ ፍጻሜያችን ድረስ እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ አንድነት ይጠብቀን ዘንድ ስለ አንድነታችን እንማልዳለን። የሚለው ዘወትር በሥርዓተ ቅዳሴያችን የምንጸልየው ጸሎት ትርጓሜው ምን ማለት ይሆን ግን …?!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!    

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

·         የ2008 ዓ.ም በዓለ ስቅለት በእመቤታችን ቀን ውሏል። እናም ይሰገዳል? ወይስ አይሰገድም?
·         ይኸው ገጠመኝ በ1913 ዓ.ም ተከስቶ በነበረበት ወቅት አበው ጉዳዩን እንዴት ፈቱት?
(መምህር ጳውሎስ መልክአ ሥላሴ):- በተወሰኑ ዓመታት መካከል የስቅለት ዕለት በየጊዜው ዘንድሮ እንደሆነው ሲገጥም ክርክር ይነሳል። አስታውሳለሁ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪ ሳለሁ እንዲሁ ስግደት በእመቤታችን ዕለት በመዋሉ ምክንያት በተለያዩ አድባራት ተበታትነን በዓሉን የምናሳልፍ ተማሪዎች እንደየደብሩ አለቃ ስሜት ወይም ግንዛቤ አሳልፈን ተመልሰናል። ማለትም አንዱ ጋር ይሰገዳል አንዱ ጋር አይሰገድም። ይህ ክርክር ዘንድሮም ቀጥሏል። ቅዱስ ሲኖዶስ የማያዳግም ምላሽ ቢሰጥበት መልካም ነው። በቅድሚያ ጾሙን በጥሩ ሁኔታ የቻላችሁትን ያክል በትጋት ላሳለፋችሁ ሁሉ እግዚአብሔር ድካም ባለው ተጋድሎዋችሁ ቸርነቱን አክሎበት የልባችሁን መሻት ይስጥልኝ። የጾምና ጸሎታችሁም በረከት ይድረሰን ለብርሃነ ትንሳኤውም በሰላም ያድርሰን እላለሁ።
ወደ ተነሳሁበት ጉዳይ ስመለስ ዘንድሮ ስቅለት በእመቤታችን ቀን ውሏል። እናም ይሰገዳል? ወይስ አይሰገድም? በሕማማት ውስጥ ከትንሳኤ በፊት ያለችው ቅዳሜ የተሻረች ሰንበት ትባላለች (ቀዳሚት ስዑር) ሃይማኖተ አበው እንደሚያዝዘን በቅዳሜ ቀን መጾም ክልክል ነው። ከቀዳሚት ስዑር በቀር ይላል ስለተሻረች የሕማማትን ቅዳሜ እንጾማታለን በሕማማት ውላለችና። ልክ እንደዚሁ በሕማማት ማንኛውም በዓል ቢውል አይከበርም።
የእመቤታችን በዓል ስለሆነ ስግደት የለም ካልንና ካልሰገድን ቅዳሴ ሊኖር ይገባ ነበር። ቅዳሴ ሳይቀደስ የሚከበር የእመቤታችን በዓል የለንምና ስለዚህ የነገው አርብ ይሰገዳል። ይህ የኔ አሳብ አይደለም የአባቶቼ ትምህርት እንጂ። እስቲ የዛሬ ዘጠና አምስት ዓመት ገደማ ስቅለት እንደዛሬ ውሎ የተፈጸመውን ክስተት ላቅርብላችሁ። የታሪኩ ጸሐፊ ክቡር ብላታ መርስዔ ኀዘን ወልደቂርቆስ ናቸው። ዓመተ ምህረቱም ሚያዝያ ፳፩ ቀን ፲፱፻፲፫ ዓ.ም( ሚያዝያ 21/ 1913 ዓ.ም ነው)። ምንም ያልተጨመረበትና ያልተቀነሰለት ታሪኩ እንዲህ ይላል።

“የስቅለት በዓል በዚህ ዘመን ሚያዝያ ፳፩ ቀን ላይ ውሎ ነበር። የአዲስ አበባ አድባራት ሊቃውንትም እኩሌቶቹ በማርያም በዓል ምክንያት ስግደት መስገድ አይገባም ሲሉ እኩሌቶቹ መስገድ ይገባል ብለው ነበርና የአሳብ ልዩነት ተፈጥሮ ዋለ።
ግርማዊት ንግሥትና ልዑል አልጋወራሽ በሚገኙበት ቤተ ክርስቲያን በሥዕል ቤት ኪዳነ ምህረት (በዓታ ያለችውን ኪዳነ ምህረት ነው) ባንድ ወገን መምህር ደስታ “መስገድ አይገባም ሲሉ” ግማሹ ሕዝብ እሳቸውን ተከትሎ አንገቱን ብቻ ጎንበስ እያደረገ ጸሎቱን ያደርስ ጀመር። እሳቸው ለማስረጃ ያቀረቡትም “መቅድመ ተአምር የማርያምን በዓላት እንደ እሁድ ሰንበት አድርጋችሁ አክብሩ ይላልና በእሁድ ቀን ምን ጊዜም ስግደት ስለሌለ ዛሬ መስገድ አይገባም” የሚል ቃል ነው።
በሁለተኛው ወገንም አለቃ ገብረ መድኅን “ስግደት መስገድ ይገባል” ስላሉ ግማሹ ሕዝብ እሳቸውን ተከትሎ ይሰግድ ጀመር። ለማስረጃም ያቀረቡት “የዛሬው በዓል በስግደት የሚከበር በዓል ነው። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታ በተሰቀለበት ቀን በመስቀሉ ስር ቆማ እያለቀሰች እና እየተጨነቀች በብዙ ድካም የዋለችበት ቀን ነው። ከዚህም በላይ ከእመቤታችን በዓል ይልቅ የክርስቶስ በዓል ይበልጣልና እንደ አበው ሥርዓት በዓሉ በስግደት ሊከበር ይገባል” የሚል ነበር። ይህ የአለቃ ገ/መድኅን አሳብ በትልቁ መምህር በአለቃ ወልደማርያም የጊቢ ገብርኤል አለቃ ሲደገፍ
የመምህር ደስታም አሳብ በሌሎች አለቆች ተደገፈ።
ከዚህም በኋላ ግርማዊት ንግሥትና ልዑል አልጋወራሽ ይህን የሊቃውንቱን ልዩነት ለማስቀረት እና አንድ ነገር ለማስወሰን ስለፈለጉ ወደ አቡነ ማቴዎስ ሁለት መልእክተኞችን ላኩ። እነርሱም የንግሥት መምህረ ንስሐ መላከ ገነት ተድላና የልዑል አልጋወራሽ መምህረ ንስሐ አባ ወልደማርያም ናቸው። እኔ ራሴ አባ ወልደማርያምን ተከትዬ ሄጄ ነበርና የሆነውን ሁሉ በቅርብ ተከታትዬዋለሁ።
መልክተኞቹ ከሊቀ ጳጳሱ ፊት ቀርበው የነገሩን አኳኋን ካስረዱ በኋላ በዛሬው ቀን ይሰገድ እንደሆነ ወይም አይሰገድ እንደሆነ ለመጠየቅ እና ውሳኔዎን ለመቀበል መጥተናል ብለው ተናገሩ። አቡነ ማቴዎስም ያለምንም ማመንታት ለአልጋወራሽ አሳወቋቸውና ይሰገድ ጀመረ።
የሆነው ሆኖ አብዛኛው ሰዓት በክርክርና በጥያቄ ምክንያት ባክኖ ነበር። እኔም ይህን ታሪክ መጻፌ ወደፊት የዚህ ዓይነት ነገር ቢያጋጥም ማስታወሻ እንዲሆን በማሰብ ነው።”
ምንጭ።- መርስዔ ኀዘን ወልደቂርቆስ “የሃያኛው ክ.ዘ. መባቻ የዘመን ታሪክ ትዝታዬ ካየሁትና ከሰማሁት” (1896-1923 ገጽ 237/38።)
++++++
ቸር ወሬ ያሰማን፣
አሜን
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

ሕዝብና መንግሥት እንዲወያዩ ጥሪ ቀረበ፤ ጸሎትና ምሕላ ታወጀ፤ ስለ ሶሻል ሚዲያና ድርቁ ማሳሰቢያ ተሰጠ!
 (ደጀ ሰላም፤ ማርች 9/2016፤ የካቲት 30/2008 ዓ.ም )፦ የብፁዕ አቡነ ናትናኤልን እረፍትና ቀብር ተከትሎ ከየሀገረ ሰብከታቸው የመጡ አበው የቅ/ሲኖዶስ አባላትን መሰባሰብ ተከትሎ የተጠራው አስቸኳይ ጉባኤ እንደተካሄደ መዘገቡ ይታወሳል። የተሐድሶ ድረ ገጾች “ማህበረ ቅዱሳን ያስጠራው ስብሰባ ነበረ፤ ከሸፈ” ሲሉ ኦርቶዶክሳውያን የጡመራ መድረኮች ደግሞ ፓትርያርኩ የሚያካሒዱትን የቤተ ክህነቱን አስተዳደርና አሠራር እንዲሁም የቅ/ሲኖዶስን የበላይነት የሚያስተሐቅር ርምጃ እንዲያስተካክሉ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው በሰፊው ዘግበዋል። ከመጋረጃ ጀርባ በዝግ በር ያለው እልህ አስጨራሽ ስብሰባ ካለቀ በኋላ የወጣው መግለጫ ብዙ ቁምነገሮች ይዞ እናገኘዋለን። ከነዚህም ውስጥ ሕዝብና መንግሥት እንዲወያዩ ጥሪ መቅረቡን፤ ጸሎትና ምሕላ መታወጁን፤ ስለ ሶሻል ሚዲያና ድርቁ ማሳሰቢያ መሰጠቱን ማንሣት ይቻላል።

የፖለቲካው አስተዳደር ከብረት የጠነከረ እጅ ጨምድዶ በያዘው ቤተ ክህነት ውስጥ የሚደረጉ ነገሮችን በላይላይ ንባብ ብቻ አነብንቦ ማለፍ ትክክለኛ ትርጉምን አያስገኝም። ለአገራቸውና ለሃይማኖታቸው ቁርጠኛ የሆኑ አባቶች የሚያደርጉትን እውነተኛ እንቅስቃሴ ሳይረዱ በመቅረት ያልሆነ ትርጉም ወደመውሰድ ሊመራም ይችላል። ከዚህ አንጻር ቅዱስ ሲኖዶሱ የወሰነውና ለሕዝብ ይፋ የተደረገው መግለጫ አበረታች ውሳኔዎችን የያዘ መሆኑን መገንዘብ ይገባናል።

ለአብነት ያህል፤ አሁን በአገራችን ያለውን ቅጥ ያጣ የመንግሥት ጭፍጨፋ እና የንብረት ውድመት፤ እንዲሁም የሕዝብ ተቃውሞ “በአንዳንድ ክልሎችና ከተሞች የሚታየው አለመረጋጋት ሁሉንም የሚያሳስብ ሆኖ አግኝተነዋል” ተብሎ ተገልጧል። ትርጉሙ“ውጥረቱ ከፍያለ ለውጥ ሊወልድ የተዘጋጀ አገራዊ ምጥ ነው” ማለት ነው። መንግሥት በሚዲያዎቹ ዕለት ተዕለት ሊያሳየን ከሚሞክረው ሥዕል ጋር እጅግ የተራራቀ ነው። “አይዟችን፤ አገር አማን ነው” የሚለውን ማሞኛ ሕዝቡም አባቶችም አልተቀበሉትም።

አሁን ያለው ችግር ተራ ችግር ሳይሆን ክቡር የሰው ልጅን ነፍስ እያጠፋ ያለ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶሱ ግሩም የሆነ ግንዛቤ አግኝቷል። “በተፈጠረው ሁከትና ብጥብጥ ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖቻችን የሀብትና የንብረት ውድመት፣ በተለይም የሕዝብ መገልገያ የሆኑ የእምነት ተቋማት መቃጠል የተሰማንን ሐዘን እንገልጻለን” ብለዋል። በርግጥም በየክፍለ ሀገሩ የሚኖሩ አባቶች እንደመሆናቸው ያለውን ችግር በቅርብ ያውቁታል። “ባሳለፍናቸው ሳምንታት በተከሠተው ሁኔታ ሕይወታቸውን ያጡ ወገኖች በመሪር ሐዘንና በጸሎት እናስባቸዋለን” ማለታቸው የሕዝቡ ስቃይ ምን ያህል እንደተሰማቸው ማሳያ ነው። መፍትሔውንም አጠይመው ለመግለጽ “ሁላችሁም ልጆቻቸን መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ወንድ፣ ሴት፣ ወጣት፣ ሽማግሌ ሳትሉ ችግራችሁን ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለሚመለከተው እንድታቀርቡ፣ መንግሥትም የሕዝቡን ችግርና ሰላማዊ ጥያቄ በመገንዘብ መፍትሔ በመስጠትና ሰላም ለማምጣት እያደረገ ያለውን የዕለት ከዕለት ጥረት እንዲቀጥልበት” ጥሪ ማቅረባቸውን ልብ ይሏል። በርግጥ የሕዝቡን ሰላማዊ ጥያቄ በጭካኔ እየጨፈለቀ ያለው ማን መሆኑ ጠፍቷቸው አይደለም። ነገሩን ለማጠየም መሞከራቸው እንጂ።

ሌላው ይበል የሚያሰኘው የመግለጫቸው አካል መንግሥት ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ረሃብ እንደሌላ ለማሳመን የሚዳክርበትን የችጋሩን ጉዳይ ያቀረቡበት መንገድ ነው። “ሕዝባችንና ሀገራችን በርኀብ፣ በድኅነትና በበሽታ ቸነፈር በተቸገረበት ወቅት” የሚለው ሐረግ ብዙ ይናገራል። “ቸነፈር” ተራ ቃል አይደለም። ከባድ በሽታን የሚወክል ቃል ነው። የረሃቡንና የችጋሩን ጽኑዕነት በበሽታው ቃል ለማስቀመጥ የሞከሩ እንጂ ይህንን ያህል ከባድ የሆነ በሽታ ገብቶ ስለርሱ ለመናገር የፈለጉ አይመስልም።

ሶሻል ሚዲያው በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ውስጥ አንድ ቦታ አግኝቶ የመግለጫ አካል ለመሆን በቅቷል። የሶሻል ሚዲያውን ሁኔታ በንቃት የሚከታተሉ ብዙ ብጹዓን አባቶች እንዳሉ ግልጽ ነው። የሚጻፈውንና የሚነገረውን ነገር በቅጡ ይገነዘባሉ፤ የሕዝቡንም የልብ ትርታ ያውቃሉ ማለት ነው። በርግጥ ፈር የለቀቁ አንዳንድ አፍራሽ የሶሻል ሚዲያ እንቅስቃሴዎች እንዳሳሰቧቸውም ግልጽ ነው። “ኅብረተሰቡን የሚለያይና የሚያራርቅ መረጃ (ኢንፎርሜሽን) ዕለት ዕለት ብታስነብቡት ትርፉ መራራቅን እንጂ መቀራረብን፤ መለያየትን እንጂ መግባባትን አያመጣም” ማለታቸው በግርድፉ ስናየው ትክክል ነው። ይሁን እንጂ ሶሻል ሚዲያው ባይኖር ኖሮ የመንግሥትን ቅጥ ያጣ ጭፍጨፋ እና ኢሰብዓዊ ተግባሮች ልንረዳ የምንችልበት ምንም አጋጣሚ አይኖርም ነበር። ስለ ጭፍጨፋው አትናገሩ ሳይሆን ጭፍጨፋውን አቁሙ የሚለው መፍትሔ ትክክለኛ ይሆናል።

በአጠቃላይ ብፁዓን አባቶቻችን ያስተላለፉት ውሳኔ ይበል የሚያሰኝ እና ከዚህ ቀደም በጉባኤ እየተናገሩ በመግለጫ ላይ ግን እንዳይገለጽ የሚጣልባቸውን ገደብ አልፈው ሐሳባቸውን ለምእመናቸው ለማድረስ መጣራቸውን የሚያሳይ ትልቅ እመርታ ነው። ቅዱስ ፓትርያርኩ ከአበው ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ቢሠሩ እና ምእመናቸውን ከክፉ ለመታደግ ቢሞክሩ ያስመሰግናቸዋል። ከዚህ በፊት እንጀመሩት በማፍረስ ተግባራቸው ቢገፉም የራሳቸውን ስምና ታሪክ ከማጉደፍ ያለፈ የሚያመጡት ለውጥ እንደማይኖር ከቀዳሚያቸው ሊማሩ ይገባቸዋል። ምእመናንም አባቶቻቸው የሚናገሩትን ንግግር ምንነት ለመረዳት በመጣር፣ እነርሱ ያሉበትን ችግር በመገንዘብና አባቶቻቸውን ለመርዳት በመሞከር የልጅነት ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባቸዋል። ፈረንጆች “reading between the lines” እንደሚሉት ከተጻፈው ነገር በላይ ያለውን ትርጉምም ለመረዳት መሞከር ይገባቸዋል። “ፊደል ይገድላል ትርጓሜ ያድናል” እንዲል። ዘመኑን በተርታ ንባብ ሳይሆን በትርጉም እንረዳው።

ቸር ወሬ ያሰማን፤

አሜን      

================== የመግለጫውን ሙሉ ቃል ከዚህ እንደሚከተለው ማንበብ ይቻላል። ======

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

“ኅሡ ሰላማ ለብሔር እስመ በሰላመ ዚአሃ ይከውን ሰላምክሙ”

(የአገርን ሰላም እሹ ፈልጉ የአገራችሁ ሰላም የእናንተ ሰላም ነውና)

 የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የሀገርና የወገን ፍቅር ያለው ሕዝብ፥ ሰላም ከእግዚአብሔር መሆኑን ያውቃል፤ ሰላም ለሰው ልጆች ከማናቸውም መሠረታውያን ፍላጎቶች በላይ ተቀዳሚ ጉዳይ ነው፡፡

ኢትዮጵያ ሀገራችን የተለያዩ ሃይማኖቶች፣ ብሔር፣ ብሔረሰቦች ተቻችለውና ተረዳድተው የሚኖሩባት የዓለም ምሳሌ ናት፡፡ ይህን ዓለምን የሚያስደንቅ ገጽታችንን ማንኛውም ኢትዮጵያዊ እንዲከተለው ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያን፣ ኢትዮጵያውያት፤

ኢትዮጵያ አህጉረ ሰላም (የሰላም አገሮች) ከሚባሉት ከዓለም አገሮች አንዷ ስትሆን በአሁኑ ጊዜ በአንዳንድ ክልሎችና ከተሞች የሚታየው አለመረጋጋት ሁሉንም የሚያሳሳብ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

ከዚህም ጋር ባለፍናቸው ሳምንታት በተከሠተው ያልተጠበቀ ችግር፡

1.በአንዳንድ አካባቢ የሰው ሕይወት ሲጠፋ፤ ትምህርት ቤቶች ሲዘጉ፤ የንግድ ተቋማት፣ የሕዝብና የመንግሥት ንብረት ሲወድም፤ የሕዝባችን የዕለት ከዕለት ኑሮ ሲናጋ ሁሉም ኅብረተሰብ የችግሩ ተጠቂ ሆኗል፤ የዚህ ዓይነቱ ድርጊት በዚህ ሁኔታ ከቀጠለ የሕዝባችን ህልውናና የትውልዱም የወደፊት ዕድል አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችላል፡፡

2.ባሳለፍናቸው ሳምንታት በተከሠተው ሁኔታ ሕይወታቸውን ያጡ ወገኖች በመሪር ሐዘንና በጸሎት እናስባቸዋለን፡፡ ስለዚህ ሁላችሁም ልጆቻቸን መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ወንድ፣ ሴት፣ ወጣት፣ ሽማግሌ ሳትሉ ችግራችሁን ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለሚመለከተው እንድታቀርቡ፣ መንግሥትም የሕዝቡን ችግርና ሰላማዊ ጥያቄ በመገንዘብ መፍትሔ በመስጠትና ሰላም ለማምጣት እያደረገ ያለውን የዕለት ከዕለት ጥረት እንዲቀጥልበት በቤተ ክርስቲያናችን ስም እናሳስባለን፡፡

3. ሕዝባችንና ሀገራችን በርኀብ፣ በድኅነትና በበሽታ ቸነፈር በተቸገረበት ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድነት መሠረታዊ ወደሆነው የልማት የሰላምና የድርቅ ጉዳይ በማተኮር መልስ ሰጭ መሆን ይገባዋል ብለን በጽኑ እናምናለን፡፡

4. ወገኖቻችን ሆይ፣ በአሁኑ ጊዜ የወቅቱ የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ (ብሎገሮችና የፌስቡክ) ተጠቃሚዎች በሙሉ ኢትዮጵያውያን ከሞያችሁ ከዕውቀታችሁ ተጠቃሚዎች የመሆን ምኞታቸው የላቀ ነው፡፡ ሆኖም መልካሙንና ለዕድገት የሚያግዛቸውን ዕውቀት እንጂ ኅብረተሰቡን የሚለያይና የሚያራርቅ መረጃ (ኢንፎርሜሽን) ዕለት ዕለት ብታስነብቡት ትርፉ መራራቅን እንጂ መቀራረብን፤ መለያየትን እንጂ መግባባትን አያመጣም፤ ከዚህ አንጻር የእናንተም ጥረትና ድካም ከንቱ ሆኖ ይቀራል፡፡ በመሆኑም የተከበረ ዕውቀታችሁን፣ ሞያችሁን፤ ለሕዝባችን ፍቅርና አንድነት፤ ለሀገራችን ሰላምና ዕድገት እንድታውሉት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትጠይቃለች፡፡

የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያን፤

ተቻችሎና ተረዳድቶ የመኖር የተቀደሰ ነባር ባህላችንን የሚያጎድፍ ማናቸውንም አስተሳሰብና እንቅስቃሴ በአንድነት መቋቋም እንደሚገባ አበክረን እየገለጽን፣ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ወገኖቻችን በሙሉ፣ በተለይም አገር ተረካቢ ትውልድ የሆናችሁ ወጣቶች፣ ሁከትና ብጥብጥብን ከሚያስከትሉ መጥፎ ድርጊቶች እንድትቆጠቡ፤ ለአገር ሰላምና ልማት ጠንክራችሁ እንድትቆሙ በልዑል እግዚአብሔር ስም አጥብቀን እያሳሰብን በተፈጠረው ሁከትና ብጥብጥ ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖቻችን የሀብትና የንብረት ውድመት፣ በተለይም የሕዝብ መገልገያ የሆኑ የእምነት ተቋማት መቃጠል የተሰማንን ሐዘን እንገልጻለን፡፡

ይልቁንም ከሁሉም በላይ ሁሉን ማድረግ የሚችል እግዚአብሔር አምላካችን፤ ለኢትዮጵያ ለሀገራችን ሕዝቦች ሰላሙን፣ ፍቅሩን፣ አንድነቱን ይስጥልን ዘንድ፤ ድርቁን ረኀቡን አስታግሦ መጪው ጊዜ ዝናመ በረከቱን ይሰጠን ዘንድ በያዝነው በዐቢይ ጾም ሱባኤ ጸሎተ ምሕላ በመላ ሀገሪቱ ባሉት ገዳማትና አድባራት የገጠር አብያተ ክርስቲያናት እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያን ይባርክ::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ

የካቲት ፳፱ ቀን ፳፻፰ ..

አዲስ አበባ

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

·        በስደት በሚገኙ አባቶች ጉባኤ አድርገው መግለጫ አውጥተዋል፤

·        “የቤተ ከርስቲያን ችግር” ያሉት በርግጥ ችግር ነውን?

·         ከመካከላቸው ያሉትና በእምነታቸው ነቅ የሌለባቸው አባቶች ለምን ዝምታን መረጡ?

·        “በስደት ባለው ሲኖዶስ ሥር ላሉ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮችና ምእመናን” ከፍ ያለ ታሪካዊ ጊዜ ነው፤

 (ደጀ ሰላም፤ ማርች 6/2016፤ የካቲት 27/2008 ዓ.ም )፦ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት እና በዋናው ጠቅላይ ቤተክህነት ስር የሚገኙ የተለያዩ ካህናት “ጊዜው ተመችቶናል” በሚል ጦርነት በከፈቱበት በዚህ ወቅት በስደት በሚገኙ አባቶች የሚመራው ቤተ ክህነት አባላት የሆኑ ካህናትም ሰሞኑን ጉባዔ ማድረጋቸውንና የአቋም መግለጫ ማውጣታቸውን አስታውቀዋል (መግለጫውን በመጨረሻ ያገኙታል):: እነዚሁ “ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ” በሚባለውና በ4ኛው ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ በሚመራው ክፍል ሥር የሚገኙ ካህናት ያደረጉት ጉባዔ ከየካቲት 21-25/2008 ዓ.ም (ከፌብሩዋሪ 29 እስከ ማርች 4/2016 መሆኑ ነው) ድረስ የተካሄደ መሆኑን “ቆሞስ አባ ጽጌ ድንግል ደገፋው፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ” በሚል ፊርማና ማኅተም የወጣው መግለጫ ያትታል። ታዲያ ስለምን ተነጋገሩ? ውሳኔያቸውስ ምን ይሆን?

በሦስት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ትምህርት መሰጠቱን ከባለ 4 ገጹ መግለጫ ለማወቅ ተችሏል። “1ኛ. “ትምህርተ ኖሎት”፤ 2ኛ.  “የቤተ ክርስቲያን ፈተና ትላንት እና ዛሬ”፤ 3ኛ. “አምልኮተ እግዚአብሔር እና ሥርዓቱ” በሚሉ ርዕሶች። አስተማሩ የተባሉት እነማን መሆናቸውን መግለጫው ባይጠቅስም ያወጡትን የጋራ መግለጫው በስምንት ቁጥሮች ከፍሎ አቅርቧል። ቁጥር 1 የመግለጫው አካል “ራሱን ማኅበረ ቅዱሳን ብሎ የሚጠራው አካል” በስደት የሚገኙ አባቶች ላይ (በስም ጠቅሶ ደግሞ ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ ላይ) “በቅርቡ በጀመረው የስም ማጥፋት ዘመቻ፣ በማን አለብኝነት የመከፋፈል ሥራ እየሠራ ይገኛል” ሲል ይከሳል።

በሰሜን አሜሪካ በመካሄድ ላይ ያለውን “ጸረ ተሐድሶ የስልክ ጉባዔዎች” የማኅበረ ቅዱሳን ጉባዔ ነው በሚል በስሕተት ወይም ደግሞ ሆን ብለው “ጠላት መጣባችሁ” በሚል ምዕመናንን ለማስተባበር የተጠቀሙበት ሊሆን እንደሚችል መገመት ቢቻልም ማኅበረ ቅዱሳን “በቅርቡ የስም ማጥፋት ዘመቻ ያደረገው” የት እና በምን ሁኔታ ነው የሚለውን ምንም አላብራሩም።

በቁጥር ሁለት መግለጫቸውም ከላይ በቁጥር አንድ የጀመሩትን በማብራራት “በየአጥቢያችን የተሰገሰጉ የማኅበሩ አባላት ረብሻዎችን ሊያስነሱብን ነው” የሚል ሥጋታቸውንና ጭንቀታቸውን ገልጸዋል። ቁጥር ሦስትም የዚያው ተጨማሪ ሆኖ ማኅበረ ቅዱሳን ላይ ያነጣጠረ ውንጀላቸው እስከ ቁጥር 6 ድረስ ይዘልቃል። በሐሳብ ደረጃ ስንመለከታቸው የመግለጫው ፍሬ ሐሳቦች በአዲስ አበባ ሀ/ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት ውስጥ ባሉ ሙሰኛ እና የተሐድሶ አስተምህሮ አራማጆች ተደጋግመው የሚገለጹትን ውንጀላዎች የደገሙ ሆነው እናገኛቸዋለን።

ቁጥር ሰባት ላይ “የሐሰት ትምህርት የሚያስተምሩ፤ እኛ ክርስቲያን አይደለንም፣ ጠላት ያወጣልን ስም ነው፣” የሚሉ ያሏቸውን ሰዎች ተቃውመዋል። እንዲህ እያሉ የሚያስተምሩት እነማን እንደሆኑ፤ ማንነታቸውን እና ምንነታቸውን ምን እንደሆነ አስረግጠው ሳያስረዱ በደፈናው ይቃወማሉ። ምእመናንን ከእነርሱ ለመጠበቅ በሚል ማስጠንቀቂያ ለመስጠትም ይሞክራሉ። ስለ ማኅበረ ቅዱሳን ብቻ መግለጫ ሰጡ እንዳይባሉ ያስገቡት ይመስልባቸዋል።

በመጨረሻ፣ እንዳይቀር እንዳይቀር በሚል ጉባኤው “ራሳቸውን ተሓድሶ ነን በሚል የፕሮቴስታንቶችን ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ስም የሚያስተምሩ መሆናቸውን በሚዲያ ከለቀቁት የስሕተት ትምህርት ጉባኤው ተረድቷል” ካሉ በኋላ ጉባኤው ስለተረዳው ነገር እና ስለ አቋሙ ገለጥ አድርጎ ሳያብራራ በደፈናው “ትምህርታዊ መልስ በመስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅ ተግቶ ለመሥራት ጉባኤው ተስማምቷል” በሚል ቤተ ክርስቲያናችንን በማመስ ላይ ስለሚገኘው ተሐድሶ ለማንሣት ይሞክራሉ።

ጉባኤው ለየትኛው ጉዳይ ክብደት ሰጥቶ ተነጋገረ? ዋናው የጉባኤው ዓላማስ ምን ነበር የሚለውን ለመረዳት ከስምንት ነጥቦች (መግቢያውን ሳይጨምር) መላልሶ ያነሣውን ጉዳይ መረዳት በቂ ነው። ይህንንም በማያሻማ ሁኔታ “በዚህ ዘመን ቤተ ክርስቲያናችን የተጋረጠባት ትልቅ አደጋ ምንድነው” ብሎ ይጠይቅና “ራሱን ማኅበረ ቅዱሳን ብሎ የሚጠራው ቡድን ነው” ሲል ራሱ ይመልሳል። (ገጽ 2)

ይህ ማኅበረ ቅዱሳን ላይ ያነጣጠረው ዘመቻ አስደናቂ የማይሆነው ከጉባዔው ተሳታፊዎች ቀንደኞቹ በተሐድሶ ትምህርታቸው የሚነቀፉት ሰዎች መሆናቸውን ልብ ሲሉ ነው። እነዚህ ግለሰቦች ኢትዮጵያ ከሚገኘውና በዋናው ቤተ ክህነት እግሩን አንሰራፍቶ ከተቀመጠው የተሐድሶ ክፍላቸው ጋር በመቀናጀት በአንድ ሰሞን፣ አንድ ዓይነት መግለጫ በማውጣትና ነገሮችን ከሥሩ አይመረምርም የሚሉትን ምእመን ለማደናገር ሞክረዋል።

ይሁን እንጂ እነርሱ እንዳሰቡት ሳይሆን በተለያየ የፖለቲካ አመለካከታቸው በሀገር ውስጥ ያለውን መንግሥት የሚቃወሙ፣ በፓትርያርክ አባ ማትያስ የሚመራውን ቤተ ክህነት እና ራሳቸውን ፓትርያርኩንም የማይቀበሉ እየመሰሉ ነገር ግን እጅና ጓንት ሆነው እንደሚሠሩ በትክክል አሳይተዋል። በቤተ ክርስቲያናችን የተፈጠረው የአባቶች ልዩነት እና ሁለት ሲኖዶስ የሚባል ችግር እንዳይቀረፍ በዚህም በዚያም ሆነው የሚያከላክሉ ሰዎችን በተሐድሶ ጉዳይ ላይ አብረው ሲሰሩ መመልከታችን “ግርግር ለሌባ ያመቻል” የሚለውን ተረት አስታውሶናል። በአባቶች መለያየት ያተረፈው አካል ማን መሆኑ ግልጽ እየወጣ ነው።

ሌላውን ትልቅ ቁምነገር “በርግጥ የቤተ ክርስቲያናችን ትልቁ ችግር በቃ ይኸው ነው? የገዳማት መበተን፣ የመምህራን መቸገር፣ የምእመናን ቁጥር ከጊዜ ጊዜ እየቆረቆዘ መምጣት፣ የአጽራረ ቤተ ክርስቲያን መጠንከር፣ የምእመናን በዘረኛ መንግስት ቁም ስቅላቸውን ማየት፣ ከቀዬያቸው መፈናቀል፣ መታሰር፣ መገረፍ እና መገደል፤ የቤተ ክህነት አስዳደርን የጨበጡ ብዙ ሙሰኛና ዘራፊ ሰዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብት በጠራራ ፀሐይ መዝረፋቸው ወዘተ እንደ ችግር እንዴት ሳይታያቸው ቀረ?

በዓላማ የተሐድሶን እምነት የሚያስፋፉትና በዚህ ጉባኤ ላይ መኖራቸውን በፎቶግራፎች ያየናቸው ሰዎች ዓላማቸው ነውና “ያስቸገረን ማኅበረ ቅዱሳን ነው” ቢሉ ብዙም አይደንቅም። ሌሎቹ አባቶች፣ በሃይማኖታቸው የማይጠረጠሩትና ወልድ ዋሕድ ብለው የሚያምኑት ግን አሁንም ዝምታን የመረጡትና አጃቢ ሆነው የቀረቡት በይሉኝታ ነው፣ ባለማወቅ ነው፣ ወይስ በርግጥም የቤተ ክርስቲያን ችግር ምንነቱን አያውቀቱትም ወይም ዘንግተውታል?

ሊሰመርበት የሚገባው ሌላው ጉዳይ በአገር ቤት ከሕወሐት ወያኔ ጋር እጅና ጓንት ሆኖ አገራችንን እና ቤተ ክርስቲያናችንን በማፍረስ ላይ ያለው የተሐድሶ ቡድን በውጪ አገር ደግሞ የተቃውሞው ኃይል አካል መስሎ ለመታየት የቻለበት ሁኔታ ነው። በዚህ ዘዴያቸው ከኢትዮጵያውያን ሬዲዮኖች እስከ ድረ ገጾች ድረስ “የነጻነት ኃይል” መስለው ለመታየት ከመቻላቸውም በላይ በፖለቲካ እያሳከሩ እምነታቸውን ለማስፋፋት በመጣር ላይ ይገኛሉ። ይህ ጽሑፍ በሚዘጋጅበት ወቅት እንኳን ይህ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ምንነት በተንሸዋረረ መልኩ ለማሳየት እና ምእመናን የአቅማቸውን እንዳያደርጉ አቅጣጫ የሚያስቀይር መግለጫ በhttp://ecadforum.com/Amharic/archives/16224/ድረ ገጽ ላይ ወጥቷል። ሌሎቹም ይከተላሉ፤ ሬዲዮኖቹም ይህንን የተሳሳተ አስተሳሰብ ሲያንጸባርቁ ይገኛሉ።

ነገ ነጻነት በኢትዮጵያ ሲመለስና ሕዝብ የመረጠው አስተዳደር ሲተከል እንኳን ዛሬ “ተቃዋሚ መስለው” የቀረቡት እነዚህ ኃይሎች ቤተ ክህነቱን ለመቆጣጠርና የአገራችንንና የቤተ ክርስቲያናችንን መከራ ለማክበድ እነሆ ተዘጋጅተዋል። ነጻነት ናፋቂው ክፍል በዚህ ጸረ ተዋሕዶ ክፍል በመታለል እስከ መቼ የአፍራሽ ተግባራቸው አካል ይሆናል?

እነሆ አሁን “በስደት ባለው ሲኖዶስ ሥር ላሉ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮችና ምእመናን” ከፍ ያለ ታሪካዊ ጥያቄ መቅረቡን ሊገነዘቡት ይገባል። ከወንዝ ልጅነት ባለፈ በመካከላቸው ያለውን ጸረ ተዋሕዶ ቡድን ሊመለከቱ ይገባቸዋል። በርግጥም አሁንም “ተሐድሶ የሚባል የለም፤ ማኅበረ ቅዱሳን ነው የፈጠረው” በሚለው ማባበያ የሚታለሉ አይመስለንም። በርግጥ ይህንን ማስጠንቀቂያ ችላ ብለው ካለፉ እጅግም ባልራቁ ዓመታት ተሐድሶ ምእመናኑን በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ ፕሮቴስታንቶች አድርጎ ያገኙታል። ያን ጊዜ ለመመለስ እጅግ ያስቸግራል። ከሕንድ ታሪክ እንማር፤ እንንቃ።

ማስጠንቀቂያ፦ በዚህ ጉባኤ ላይ የተገኙትን አባቶች በጅምላ ተሐድሶ ናቸው አለማለታችን ግልጽ ቢሆንም ደግመን ለማሳሰብ እንወዳለን። ነገር በማመሳሰል ያልተባለውን ተባለ ለሚሉት መናፍቃን ዕድል አንሰጣቸውም።

መልካም ዐቢይ ጾም

ቸር ወሬ ያሰማን፤

አሜን      

        

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

·        ከካቶሊክ ጋር ያለን ልዩነት ጠባብ ነው(አባ ማቲያስ ሕዳር 2008)

·        ከቫቲካን ጋር የነበረንን የቀድሞ ፍቅር(?) እንመልሰዋለን(አባ ማቲያስ የካቲት 2008)

·         ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስትያንን የገዛ ቅኝ ገዥ ነው(አባ ማቲያስ ጥቅምት 2008)
·        ወራሪዋን ቫቲካንን ፍቅር : ልጆቻቸውን ቅኝ ገዥ— አባት ብሎ ዝም!!

(ዘአዲስ እንደፃፉት):- አባ ማቲያስ በዚህ ዓመት ጥቅምት ወር ላይ ትግራይ ሄደው ጉብኝት ማድርጋቸው ይታወሳል:: አዲግራት ላይ የአዲግራቱ የካቶሊክ ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ቦታ ላይከካቶሊክ ጋር ያለን ልዩነት ጠባብ ነውበማለት መግለጫ መስጠታቸው ይታወሳል:: http://www.addisadmassnews.com/images/Issue-826.pdf

ሀገራዊ ማህበራዊና ብሔራዊ በሆነ ጉዳይ ላይአንተ ኦርቶዶክስ : አንተ ካቶሊክመባባሉ ሳይኖር የሁሉም እምነት ተከታይ የሆነ ኢትዮጵያዊ በአንድነት መቆም እንዳለበት ግልጽ ነው:: “ኦርቶዶክስና ካቶሊክ መካከል ያለው ልዩነት ጠባብ ነውብሎ የማይመስል ነገር መናገሩ ( ያውም ከፓትርያርኩ አንደበት) ግን እጅግ የሚያስተዛዝብና ግምት ውስጥ የሚጥል ስህተት ነው:: የሆነው ሆኖ ይህን ባሉ በሶስተኛው ወር የካቶሊኳ ራስ ቫቲካን ደርሰው የበርካታ ኢትዮጵያውያንን አንጀት አቁስለው ተመልሰዋል::

 ፓትርያርኩ ቫቲካን መሄድ ነበረባቸውን?

በመሰረቱ: ቫቲካን ኢትዮጵያና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን ላይ እጅግ የመረረ ግፍ ፈጽማለች:: ፋሺስት ጣልያን ኢትዮጵያን ስትወር : የቫቲካን ጳጳሳት የመርዝ ጋዝ እየባረኩ ኢትዮጵያን ለመውረር የሚደረገው ጦርነት ቅዱስ ጦርነት እንደሆነ አውጀዋል:: የወርቅ መስቀላቸውን ሳይቀር ለጦርነቱ አዋጥተዋል:: የሙሶሎኒምና የግራዚያኒ ቀኝ እጅ የነበረው የቫቲካኑ ጳጳስ ባደባባይ ወረራውን ደግፎ መግለጫ ሰጥቷል::

(http://www.globalallianceforethiopia.org/italianinvasion.pdf)

ፋሺስት ጣልያን አንድ በዛ ጦርነት አንድ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ገድላለች:: በሺዎች የሚቆጠሩ ካህናትን አቃጥላለች:: በውል የታወቁትን እንኳን ብንቆጥር ወደ 2 ቪህ አብያተ ክርስቲናትን አውድማለች:: ጣልያን ከመውረሯ በፊትም የጣልያን ሰላይ እየሆኑ ይሰሩ የነበሩት የቫቲካን መነኮሳት ነበሩ::

ቫቲካን ስለሰራችው ጥፋት ኢትዮጵያንን እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስትያንን ይቅርታ ለመጠየቅ ፈቃደኛ ስላልሆነች : ላለፉት አርባና ሃምሳ ዓመታት የቫቲካንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስትያናት ግንኙነት በጣም ቀዝቃዛ ነበር:: ቫቲካን ይቅርታ እስካልጠየቀች ድረስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን አባቶች ከቫቲካን ጋር አንድነት እንዳይኖር በመወሰናቸው የሁለቱ አብያተ ክርስትያናት ግንኙነት በጣም ቀዝቃዛ ነበር:: ( የአለቃ አያሌውመች ተለመደና ከተኩላ ዝምድናመጽሓፍን ይመልከቱ)

በተለይ አሁን በቅርቡ ለጨፍጫፊው ግራዚያኒ ጣልያን ውስጥ ሀውልት እንዲቆም ከተወሰነ በኋላና የቫቲካን ጳጳሳትም ይህን ጉዳይ የመደገፋቸው ዜና በመሰማቱ : በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ተቃውሞ በማሰማታቸው የሃውልቱ ስራ ቆሟል:: እነዚሁ ኢትዮጵያውያን ቫቲካን ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስትያንን ይቅርታ እንድትጠይቅ ቢወተውቱም : ቫቲካን ካላት ንቀት የተነሳ ፈቃደኛ አልሆነችም:: የሙገርመው ግን ጀርመን ናዚዎች አይሁዶችን ሲጨፈጭፉ ዝም በማለቴ ( ባልሳተፍበትም) ይቅርታ ጠይቃለሁብላ አይሁዶችን ይቅርታ ጠይቃለች::

(https://www.gopetition.com/…/vatican-apology-for-ethiopian-…)

ራሷ የጨፈጨፈችውንና ያስጨፈጨፈችውን ኢትዮጵያውያንን ግን ይቅርታ ለመጠየቅ ፈቃደኛ ባለመሆኗ : ቫቲካን ኢትዮጵያን ይቅርታ እስክትጠይቅ ድረስ ይፋዊ ግንኙነት እንዳይኖር በኢትዮጵያ በኩል ተወስኖ ነበር:: የአለቃ አያለውውን መች ተለመደና ከተኩላ ዝምድና ያነቧል::

አባ ማቲያስ ግን ያንን እግድ ጥሰው ቫቲካን ድረስ በመሄድእኛና ቫቲካን ድሮም ፍቅር ነን: የድሮውን ፍቅር እንመልሰዋለንበማለት የብዙ ኢትዮጵያውያንን ድካም መና አብልተውታል::

የአባ ማቲያስ ቫቲካን መሄድ እንግዳ ቢሆንም ብዙዎእዛው ሀገራቸው ላይ ሄደው ቫቲካን ለሰራችው በደል ይቅርታ ትጠይቅብለው ይናገራሉ ተብሎ ተጠብቆም ነበር:: በተገላቢጦሹ ግን አባ ማቲያስድሮም እኛና ቫቲካን ፍቅር ነበርን ወደፊትም ያንን ፍቅር እንመልሰዋለንብለው አረፉት::

የቀደመው የቫቲካንና የኦርቶዶክስ ፍቅር የቱ እንደሆነ አልገባኝም:: የዲዮስቆሮስ ይሆንን? ከጥንት ጀምሮ ቫቲካን የምትልካቸው ሚሺነሪዎች ሕዝብ ሲያጨፋጭፉ ነገር ሲተክሉ እንጂ ፍቅር መስርተው ሲሄዱ አይታወቅም:: እነ አልፎንሱ ሜንዴዝን መጥቀስ ይቻላል:: ቃል በቃልኢትዮጵያ ቤተ ክርስትያን ላይ ሁለት እሾክ ተክዬባት ሄድኩእስከማለት የደረሱ ናቸው:: ጸጋና ቅባትን ያስትውሷል:: ጂሴፔ ሳፔቶና አባ ማስያስም ኢትዮጵያን ለጋ ቅቤ ሲቀቡ አናቃቸውም:: በሁለቱም የጣልያን ጦርነት ወቅትም ቫቲካን የሰራችው ወንጀል እንጂ የፍቅር ስራ አይደለም:: (አቡነ ጎርጎርዮስ ////ታሪክ)

የኦርቶዶክስና የቫቲካን የቀደመ ፍቅር የቱ እንደሆን አይገባኝም:: ፓትርያርኩ እንደዛ ከሚሉቫቲካን አትፍታለችና ይቅርታ ትጠይቅ,ኢለውን ያባቶቻቸውን ቃል አጽንተው እሳቸውም ይሄን ቢያደርጉ ለነፍሳቸውም ለስጋቸውም ታሪክ ነበር:; ማኅበረ ቅዱሳንንቅኝ ገዥያለ አንደበት እውነተኛዋ ቅኝ ገዥን ምን ይላት ይሆን ብዬ ጠብቄም ነበር::

ምን ያደጋል ! አባታችን አገላበጡት

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

(ማርች 2/2016/ የካቲት 23/2008 ዓ.ም):- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ወደ ቫቲካን ጉዞ ማድረጋቸው እና ከሮማማው ፓፓ “ፖፕ ፍራንሲስ” ጋር ተገናኝተው መወያየታቸው በመገናኛ ብዙኃን ተዘግቧል፡፡ ሲጨባበጡ፣ ትከሻ ለትከሻ ተሳስመው ሰላምታ ሲለዋወጡ፣ ፓትርያርካችን ለፖፕ ፍራንሲስ ማስታወሻ መስቀል እና መጽሐፍ ሲሰጡ ሁሉ አይተናል።
የሁለቱ መሪዎች ዋነኛ የመወያያ ርዕሰ ጉዳይ በመካከለኛው ምስራቅ ያለው የክርስቲያኖች መከራ፣ ስደትና የቤተ ክርስቲያን ውድመት እንደሆነ ከፖፑ ንግግር መረዳት ይቻላል። “የክርስቲያኖች የሰማዕትነት ደም የክርስትና ዘር ነው” የሚለውን ታዋቂ ቃል አንስተው ፖፑ ማብራራታቸው ተዘግቧል። ዝርዝሩን መመልከት ለሚሻ ዜናው ወደተዘገበባቸው ሥፍራዎች ጎራ ማለት ይችላል።

ሁለቱም መሪዎች ከተሾሙ ብዙም አልቆዩም። ፓትርያርክ ማትያስ February 28/ 2013፤; ፖፕ ፍራንሲስ ደግሞ    በቀናት ልዩነት March 13/ 2013 ነው የተሾሙት። ሁለቱም መሪዎች በአማኞቻቸው የሚታዩበትን ጠባይ በአጭር ጊዜ ለመቅረጽ የቻሉ ሆነዋል። ያሳዩት ጠባይ ግን ልክ እንደ ልብሳቸው እጅግ የተቃረነና የተለያየ ነው። ፓፓ ፍራንሲስ ልጆችን በማባለግ እና በሌሎችም አስነዋሪ ተግባራት ስሟ የጎደፈውን የካቶሊክን ቤተ ክርስቲያን በጥቂት ዓመታት ውስጥ ስሟን ለማደስና በዓለም ሕዝብ ዘንድ ያላትን ተቀባይነት እጅግ በላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ችለዋል።
ፓፓው ከሠሯቸው ተግባራት መካከል አንዱ ለረዥም ዘመናት ተለያይተው የነበሩትን ኩባንና አሜሪካንን ለማስታረቅ ድልድዩን ያበጁትና ታሪክ የሠሩት እርሳቸው መሆናቸው ነው። ኮሚኒስቱን የኩባ አስተዳደር ከደመኛ “ኢምፔሪያሊስት ጠላቱ” ከአሜሪካን መንግሥት ጋር ለማግባባትና በሁለቱ ሕዝቦች መካከል የፈረሰውን የግማሽ ምዕት የግንኙነት መስመር ለመጠገን ችለዋል።
ከዚህም በላይ ፓፓው በዓለም አማኝም ኢ-አማኒም ሕዝብ ዘንድ ሞገስ ያሰጣቸው ለድሀውና ለዝቅተኛ ኑሮ ለሚኖረው ለመላው የዓለም ሕዝብ ያሳዩት ጥብቅና፤ ገንዘብ አምላኪውን የዘመናችንን ሉላዊ ሥርዓት በይፋ እየተቃወሙ ለአገሮች ኢኮኖሚያዊ ጤንነት ያሳዩት ወገንተኝነት ነው። ድህነትን እንደበሽታ ለሚጠየፉ ብዙ ቅንጡዎች እና ቅምጥሎች ትልቅ ትምህርት በሚሰጠው ተግባራቸው ከኦባማ ዋይት ሐውስ እና የአሜሪካ ኮንግረስ እስከ ደቡብ አሜሪካ የተለያዩ  አገሮች ግድ የለሽ መንግሥታት ድረስ ምክራቸውን እና ተግሳጻቸውን አሰምተዋል።
የቅምጥል ኑሮን የሕይወታቸው መመሪያ በማድረግ ረገድ ከዓለማውያኑ የባሱት መንፈሳውያን የእምነት መሪዎች በሆኑበት በዚህ ዘመን ፖፕ ፍራንሲስ የቫቲካንን ወደር የለሽ የድሎት መኪናዎች ለመጠቀም አሻፈረኝ በማለት እና እዚህ ግቢ የማትባል የግል መኪናቸውን በመጠቀም በንግግራቸውም በግብራቸው ቅምጥልነትን አውግዘዋል።

ለጉብኝት በሑዱባቸው አገሮች በአጃቢ የተሸለሙ መኪኖቻቸወን በማቆም እና በመንገድ ላይ ከሚጠብቃቸው ሕዝብ ጋር በተለይም ከሕጻናት እና የተለያየ በሽታ ካለባቸው ሰዎች ጋር በመገናኘት፣ እንኳን ለመንካት ለማየት እጅግ የሚፈትን በሽታ ያለባቸውን ሰዎች ሳይጸየፉ በማቀፍና ርኅራኄ በማሳየት ብዙዎችን አስደምመዋል። ሌሎችንም የታዘብናቸውን ብዙ ተግባሮቻቸውን መጥቀስ ይቻላል። ለዚህ ፅሑፍ ሲባል በዚሁ እንግታውና የኛው ፓትርያርክ ሊሟሯቸው ስለሚችሏቸው ነገሮች እናንሣ።

መቸም አንድ የኦርቶዶክስን አባት ከካቶሊክ መሪ “ይህንን ተማር፣ ይህ መልካም የሆነ የኮቶሊኩ መሪ ተግባር ነው” ማለት ችግር ላይ ሊጥል የሚችል ነገር እንደሆነ ይታወቃል። “ካቶሊኮችን ያመሰግናሉ” የሚል የነገረ ሰሪ ጥላሸት ሊያስቀባም ይችላል። በቀድሞው ዘመን ቢሆንማ “ሰዎቹ ኮተሎኩ” ሊያሰኝም ይችል ነበር።
ይሁን እንጂ ቅ/ያሬድ ከዚያች ትል መውደቅንና መነሣትን ተምሮና ተገንዝቦ፣ ሕይወቱን አርቆ ለቤተ ክርስቲያናችን ዓይን እንደሆነ ሁሉ የሰው ልጅም በሥላሴ አርአያ ከተፈጠረ ከሌላው ሰው (አማኝም ሆነ የማያምን፤ ኦርቶዶክስም ሆነ ካቶሊክ) መማር መቻሉ ያስመሰግነዋል እንጂ አያስነቅፈውም። ከባዶ ግብዝነትም ያድነዋል።
ወደ ቀደመ ነገራችን ስንመለስ …. ከላይ እንዳየነው ፓትርያርክ ማትያስ ከፖፕ ፍራንሲስ በቀናት ልዩነት ነው የመሪነት መንበር የተቀበሉት። ነገር ግን በነዚህ 3 ዓመታት ምን ሠሩ ብለን ብንገመግም ከፀብና ከዓምባ ጓሮ፣ በአደባባይና በሚዲያ ከሚሰጡት አሸማቃቂ ንግግር ባለፈ እንዲሁም ከቅ/ሲኖዶስ አባላት በመራቅ ቤተ ክርስቲያንን ተደራጅተው ከሚዘርፉ ሰዎች ጋር ከመወዳጀት ሌላ መልካም ስም ያተረፉ አይመስለንም።
የካቶሊኩ ፓፓ ለድሆች ጠበቃ መሆናቸውን አይተናል። የኛዎቹም ለኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ ጠበቃ ሊሆኑ ይገባቸው ነበር። በኑሮ ውድነት፣ በአስተዳደር ብልሹነት፣ በስግብግበነት መሬቱን እና ቤቱን እየተዘረፈ ትዳሩ ለሚፈርሰው ወገናቸው ጠበቃ ሊሆኑ ይገባ ነበር። ጋሻ ጃግሬዎቻቸው እርስበእርስ በመሸላለምና የቤተ ክርስቲያን ገንዘብ በገፍ በመዝረፍ በተጠመዱበት በዚህ ጊዜ “ኧረ ተዉ!!!” የሚል የአባት ተግሳጽ ሊያሰሙ ይገባ ነበር።
እንደ ካቶሊኩ ፓፓ አስታራቂ እና የተበተኑትን ሰብሳቢ መሆን ቢያቅታቸው የተሰበሰቡትን ለመበተን መትጋት ግን አይገባቸውም ነበር። በዚህ አንድ ዓመት በማኅበረ ቅዱሳን ላይ የፈጸሙትና እየፈጸሙት ያለው ተግባር ብቻ ለታሪካቸው ትልቅ ጠባሳ እንደሚሆን ሊገነዘቡት በተገባ ነበር።
በመካከለኛው ምስራቅ ለሚገደሉ ክርስቲያኖች አዝነው ሮም ድረስ እንደሔዱት ሁሉ፣ በአገራቸው ለሚጠፋው ሕዝባቸው፤ በመንግሥት ወታደር ዕለት ከዕለት እየተገደለ በየጥሻው ለሚጣለው ወገናቸው፤ ማዕከላዊን ጨምሮ በየእስር ቤቱ በማሰቃያዎች ለሚንገላታው ወገናቸው ጠበቃ መሆን ይችሉ ነበር።
ድሃ አደጉንና ዕጓለ ማውታውን ለመሰብሰብ ከአበው ሌላ ማን ይመጣል። ቤተ ክህነቱ ከገባበት አስረሽ ምቺው ተላቆና የምንኩስና አሰረ ፍኖቱን ተከትሎ ከዚህ የመንደላቀቅና የመሽቀርቀር አዚም ሊገላገል፣ ለድሃውም ሊያዝን ይገባው ነበር። የካቶሊኩን ፓፓ ካነጋገሩ አይቀር ይህንን ይህንንም ከእርሳቸው ይማሩ። ፓትርያርካችን ሆይ! በእርስዎ ዘመን ቤተ ክርስቲያናችን ስሟና ታሪኳ ይገነባል ወይስ ይፈርሳል?  
   
ቸር ወሬ ያሰማን
አሜን
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

(http://eotcmk.org):- ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐረፉ:: ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በምሥራቅ ትግራይ ክለተ አውላሎ አውራጃ አውዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አጥቢያ ከአባታቸው ከአቶ ገብረ ሕይወት ፀዓዱ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ወለተ ክርስቶስ ቢሻው በ1923 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ዲቁናን ከአቡነ ይስሐቅ፣ ቅስና፣ ቁምስና እና ምንኩስና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ተቀብለዋል፡፡

ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የትግራይ ሀገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው ተሹመዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከ30 ዓመታት በላይ የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው በማገልገል ላይ ሳሉ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም ዐርፈዋል፡፡
ሥርዓተ ቀብራቸው ሐሙስ የካቲት 24 ቀን 2008 ዓ.ም በሀገረ ስብከታቸው ራሳቸው በገደሙትና ከፍተኛ መንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጡበት በነበረው ደብር ቅዱስ ደብረ መዓዛ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ይፈጸማል፡፡
                                                                                                                  
 የአባታችንን ነፍስ ከደጋጎቹ አበው ጋር ያድርግልን
አሜን።
         
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ “ተሐድሶ” (ሪፎርሜሽን) ለማካሔድና በእነርሱ እምነት “ተባላሽቷል” የሚሉትን በመቀየር ገሚስ ፕሮቴስታንት ገሚስ ኦርቶዶክስ መሰል እምነት የመፍጠር ዓላማ መኖሩ አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው እውነታ ሆኖ “አለ ወይስ የለም?” በሚል ለምን ግር ይለናል? በሃይማኖታቸው ኦርቶዶክሳዊነት የማይጠረጠሩ ብዙ ሰዎች በዚህ ጉዳይ ልባቸው ይከፈላል። ለማመንም ለመተውም ይቸግራቸዋል። በሌላ አቀራረብ የሚቃወሙትን ኦርቶዶክሳዊ ያልሆነ ትምህርት ለማስፋፋት የሚጥሩትን ተሐድሶዎቹን ሲረዷቸው ይገኛሉ። ይህ የመደናገርና ግርታ ላይ የመውደቅ አባዜ እጅግ ሥር ከመስደዱ የተነሣ በአገር ቤት ያለችውን ቤተ ክህነት እጅግ እግሯን አስሮ ሊቆጣጠራት ምንም አልቀረውም። ከአገር ቤቱ ተገንጥለን የራሳችን ሲኖዶስ አለን የሚሉትንም አባቶች እንዲሁ መጠቀሚያው አድርጓቸዋል። የቤተ ክርስቲያናችን ፈተና የሆነው ይህ “ሪፎርሜሽን/Reformation” የተባለ አፈንጋጭ አስተምህሮ ሊያመጣ የሚችለው ውጤት ለማይታያቸው ምናልባት የዚሁ ችግር ሰለባ የሆነችውን የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በአጭሩ መጥቀስ አብነት ሊሆን ይችል ይሆን?

የሕንድ ኦርቶዶክሶች ከቅ/ቶማስ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት የሚመዘዝ ረዥም ሃይማኖታዊ ታሪክ አላቸው። ልክ እንደኛዋ ቤተ ክርስቲያን ሁሉ በ17ኛው መ/ክፍለ ዘመን ወደ አገራቸው የገቡት ፖርቹጋሎች ባመጡት “ኦርቶዶክሳውያንን ካቶሊክ የማድረግ ዘመቻ” ብዙ መከራ ተቀብለዋል። ግማሽ ሕዝባቸውንም አጥተዋል። በእነርሱ እግር የተተኩት አዲሶቹ የሕንድ ገዢዎች እንግሊዛውያን በበኩላቸው ኦርቶዶክሶችን “አንግሊካን” ለማድረግ በነበራቸው ፍላጎት በገንዘባቸው “የቲዮሎጂ ኮሌጅ በማቋቋምና ራሳቸው ረዳት መስለው በመግባት” ኦርቶዶክስ መምህራንን ሊያፈራ የተቋቋመን መንፈሳዊ ኮሌጅ ለራሳቸው ዓላማ በመቀልበስ ከፍተኛ ጉዳት አድርሰውባቸዋል። በዚህም ሰበብ “ማላባር ኢንዲፔንደንት ቸርች፤ ማላንካራ ማር ቶማ ሴሪያን ቸርች እና ሴይንት ቶማስ ኢቫንጄሊካል ቸርች” የተባሉ ሦስት የፕሮቴስታንት እምነት ክፍሎች ሊፈጠሩ ችለዋል።

ከሕንድ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደምንረዳው “ተሐድሶው” የተጀመረው በአንግሊካን እንግሊዞች እርዳታ፣ ቄስ ያውም የቲዎሎጂ መምህር በነበረ ሰው አማካኝነት ነው። ይህ “አብርሃም ማፕላን” የተባለ ግለሰብ ዘመዱ የሆነን ዲያቆን መንበረ ፕትርክናው ወደሚገኘው ወደ ሶሪያ የሐሰት ደብዳቤ አስይዞ በመላክ እና ጵጵስና እንዲቀበል በማድረግ ሐሳቡን ከግብ ለማድረስ ችሏል። ጵጵስናውን ተሳስተው የሰጡት ፓትርያርክ ነገሩ ስሕተት መሆኑን ዘግይተው ቢገነዘቡም የደረሰውን ጥፋት እና ስብራት ለመጠገን ሳይቻላቸው ቀርቷል። ችግሩን ለመፍታት ሕንድ ድረስ ቢጓዙም “የፈሰሰ አይታፈስ” ሆኖባቸው አልፏል።

ዛሬ ተሐድሶዎች በቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም ዘርፍ ተንሰራፍተው ተቀምጠዋል። በአገር ቤትም በውጪውም ሲኖዶሶች አይነኬ ከመሆን ደረጃ ደርሰዋል። የሚያራምዱት እምነት ተሐድሶ መሆኑ በሰፊው እየተነገረ ዲቁናም ቅስናም የሚሰጣቸው ጳጳስ አላጡም። ምንኩስናን እየተቃወሙ ለጊዜው የመነኩሴ ቆብ የደፉትም ጵጵስና ለመቀበል በአገር ውስጡም በውጪውም ተራ በመጠበቅ ላይ ይገኛሉ።

እነዚህ ሰዎች እንደሚፈራው እስከ ጵጵስናው ማዕረግ ለመድረስ ከቻሉ በሕንድ የደረሰው በእኛም ላይ እንደማይደርስ ምንም ማስተማመኛ ማግኘት አይቻልም። የሕንዱ ተሐድሶ (“የማር ቶማ ቸርች”) በእምነት ከአንግሊካኖች ጋር አንድ መሆኑን አውጆ የራሱን ጎጆ እንደቀለሰው ሁሉ የኛዎቹም የራሳቸውን ጎጆ የማይቀልሱበት ምንም ምክንያት የለም። በሕንዶች ከ1880ዎቹ ጀምሮ የተከሰተውን ታሪክ ከ150 ዓመት በኋላ የተፈጠርን ሰዎች ተመልክተን ችግሩን መገንዘብ ለምን ያቅተናል?

የሶሪያው ፓትርያርክ ለተሐድሶዎቹ የመጀመሪያ ጳጳስ ማዕረጉን ተሳስተው እንደሰጡት ሁሉ ዛሬም አውቀውም ይሁን ሳያውቁ መናፍቃኑን ማዕረግ በማዕረግ አድርገው በመንጋው ላይ በእረኛ ፈንታ ተኩላ የሚልኩባቸው ሰዎች ከፍ ያለ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባቸው ነበር።

በዚህ ወቅት የተሐድሶዎች ክፍል በቤተ ክህነቱ የተፈጠረው የአባቶች መከፋፈል ሰርግና ምላሽ ሆኖት ከዚህ ሲሉት ከዚያ፣ ከዚያ ሲሉት ከዚህ እያጣቀሰ ስሩን እያስፋፋ ሲሆን የአባቶች መከፋፈል እውነት የመሰለው ኦርቶዶክሱ ክፍል በዚህም በዚያም ወገን እየተጎዳ ከሁለት ያጣች ጎመን ሆኖ ተዘልሎ ተቀምጧል። የተሐድሶው ክፍል አገር ቤት ሲገባ ኢሕዴግን፤ ውጪ ሲወጣ ተቃዋሚውን እየመሰለ ዋና ዓላማው የሆነውን የኑፋቄ ስራ በሰፊው ያስፋፋል። “ፓትርያርካችን አቡነ መርቆርዮስ ናቸው” ሲል ይቆይና አቡነ ማትያስ የደገፉት ሲመስለው ተቀልብሶ ሲያመሰግናቸው ያመሻል። “አቡነ ማትያስ ፓትርያርኬ” ሲል የቆየው አገር ቤት ያለው ክንፋቸው ሲመቸው ደግሞ ውጪ ያሉት አባቶች ጋር ራት ሲበላ ይገኛል። በዚህም በዚያም ግን ቤተ ክርስቲያን እየደማች ነው። ይህ አዚም የሚለቀን መቼ ነው? የምንደናገረውስ እስመቼ ነው?

በዚህ ረገድ ፓትርያርክ አባ ማትያስ ቀደምቶቻቸው አድርገውት በማያውቁት መጠን እና ስፋት ቤተ ክርስቲያኒቱን ጅብ እያስበሏት ነው። አውቀውትም ይሁን ሳያውቁት የተሐድሶዎችና የዚሁ ዓላማ መጋቢ የሆኑ ግብረ በላ ወዳጆቻቸው መጠቀሚያ ሆነዋል። በቤተ ክህነቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚያስብል ደረጃ ከቅ/ሲኖዶስ ተነጥለው፣ ሲኖዶሳዊቱን ቤተ ክርስቲያን ኢ-ሶኖዶሳዊ አስተዳደር ተክለውባታል። ብዙ ሚሊዮን ሕዝቧ በረሃብና በችጋር የዓለም መሳቂያ መሳለቂያ በሆነበት ዘመን፤ የኑሮ ምሬት ያንገሸገሸው ሕዝብ ከሰሜን እስከ ደቡብ ግዛቶች ምሬቱን በሚያሰማበትና በዚሁ ሰበብ የሚያልቀው ምእመን የቀብሩን ስፍራ ባጣበበት በዚህ ወቅት “አስረሽ ምቺው” የቅንጦትና የዘረፋ ሰደድ ቤተ ክህነቱን አቀጣጥሎታል። ይህ ሁሉ ሰርግና ምላሽ የሆነው ግን ለተሐድሶው ኑፋቄ ነው። ይህ ሁሉ ነገር እንዴት ያደናግረናል? ለምንስ አንነቃም?

                                               

ቸር ወሬ ያሰማን፤

አሜን። 

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

(በፀሐፊው ፈቃድ ከፌስቡክ ተወስዶ የተለጠፈ)፦ ዛሬ ግንቦት 27 30ኛው የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እንደሌሎቹ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርኮች ሁሉ ይህንን አባትም የትሩፋቱንና የዕውቀቱን ዜና በሰሙ ጊዜ በእስክንድርያ አገር ያለፍቃዱ ይዘውት ሊቀ ጵጵስና ሾሙት፡፡ የዕለቱ ስንክሳርወደረሰ ድርሳናተ ብዙኃተ ወአቀመ እግዚአብሔር በመዋዕሊሁ ቀርነ ቤተ ክርስቲያንእንዲል በዘመነ ፕትርክናውም ብዙ ድርሳናትን የደረሰና የቤተ ክርስቲያንን ስልጣን ያጸና አባት ነው፡፡

በዚሁ ዕለትም የማርያምና የማርታ ወንድም የሆነውና ጌታችን ከሞት እንዳስነሳው በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 11 ታሪኩ በሰፊው የተጻፈው አልዓዛር የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ይህ አልዓዛርም ጌታ ካስነሳው በኋላ ከሐዋርያት ጋር የአጽናኝ መንፈስ ቅዱስን ጸጋ የተቀበለ እና በኋላም ሐዋርያት እጅ በመጫን በቆጵሮስ አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት የሾሙት ነው፡፡ እርሱም መንጋውን በመልካም አጠባበቅ ጠብቆ በሹመቱ አርባ ዓመታትን ኑሮ በሠላም አረፈ፡፡አረፈየተባለለትም ይኼኛው ዕረፍቱ እንጂ ወደእግዚአብሔር ከመመለሱ በፊት፣ ለአገለግሎት ከመጠራቱ በፊት፣ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከመቀበሉ በፊት እንዲሁም የተሰጠውን የክህነት አደራ ከመወጣቱ በፊት የሞተውሞቱንአይደለም፡፡
እንደቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን እኛም እነዚህን ሶስት ነገሮችን በአባቶቻችን ዘመነ ፕትርክና ለማየት እንናፍቃለን፡፡ እነዚህም ለፍቅረ ሢመት ግድ ሳይኖራቸው ነገር ግን ትሩፋታቸውና ዕውቀታቸው ብቻ ታይቶ ለቤተ ክርስቲያን ይጠቅማሉ ተብለው ሳይወዱ በግድ የሚሾሙ የተሾሙት ለሥራ መሆኑን አውቀው በቃል በመጽሐፍ ምዕመኑን በማስተማር የሚተጉ፣ እንዲሁም በዘመነ ሢመታቸው ሁሉ የክርስቶስን መንጋ በመልካም አጠባበቅ የሚጠብቁ ኤጲስቆጶሳትንና ሊቃለ ጳጳሳትን፡፡
ካህናት አባቶቻችን ሳይወዱ ተገድደው በትሩፋታቸውና ዕውቀታቸው ብቻ የተገባቸው ሆነው ኤጲስቆጶስነት ሹመት የሚበቁበትን ጊዜ የማይናፍቅ እውነተኛ ምዕመን የለም፡፡ በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ ቦረዳ ገዳምን በአበምኔትነት እያስተዳደሩ እንዳሉት አባት ከአንዴም ሁለቴ ለኤጲስቆጶስነት ታጭተውተውኝ እኔ እዚሁ ጸሎት እያደረኩ ልኑርብለው እምቢ ያሉ ጥቂት ደጋግ እና ቀና አባቶች በዘመናችንም ቢኖሩም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በመጣ ቁጥር ሳይገባቸው ለኤጲስቆጶስነት ሹመት የሚቋምጡና ለዚህም በሥራ ዘርፉ የተሰማሩ እበላ ባዮችን ኪስ እንደሚያደልቡ በተደጋጋሚ የምንሰማው ለጆሮ ግን የሚሰሰቀጥጥ ወሬ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ባልደረሰ የምንልበት ደረጃ ላይ አድርሶናል፡፡
በተጨማሪም የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርኮችን ዜና ዕረፍት ስናነብ የብዙሃኑበዘመኑም ሕዝቡን በመልካም አጠባበቅ ጠብቆ በሠላም አረፈይላል፡፡ የእኛስ አባቶች ምን ያህል በበጎ አጠባበቅ ጠብቀውን ይሆን? እርግጥ ነው ለእረኞቻችን የምናስቸግር በጎች እንኖራለን፡፡ ነገር ግን የእኛ እረኞች የሆኑት እነዚህ አባቶችስ ምን ያህል ያስቸገርነውን እኛን ለማቃናት ሞክረዋል? ለስንቶቻችንስ አመጸኛነት ድጋፍ ሰጪ ሆነዋል? ስንቶቻችንን ከተሳሳትንበት መንገድ መልሰውናል? ለስንቶቻችንስ ከመንገድ ፈቀቅ ማለት በአንድም በሌላም ዓይነተኛ ምክንያት ሆነዋል? ስንቶቻቸውስ ከእውነት ጎን ተሰልፈው መንጋውን በመልካም አጠባበቅ በመጠበቅ ክፉ ዘመንን ለማሳለፍ ተግተዋል? ስንቶቻቸውን የበጎቹን ዘመን እጅግ እንዲከፋባቸው አድርገዋል? ስንቶቻቸውስ የተረከቡትን የእረኝነት አደራ እና የገቡትን ቃል አክብረዋል? ስንቶቻቸውስ ለእውነተኛቹ አባቶች እንደሚገባ በጸሎት በመትጋት መንጋቸውን ከሚያገሳው አንበሳ ከዲያብሎስ ጠብቀዋል? ስንቶቻቸውስ በምድር ያለች የእግዚአብሔር መንግሥት ለሆነች ለቤተ ክርስቲያንን ልዕልና በጽናት ቆመዋል? ስንቶቻቸውስ ይህንን መንፈሳዊና ሰማያዊ እንዲሁም ክርስቶሳዊ ኃላፊነት ወደኃላ ችላ ብለውታል
እንደ አገባቡ ከሆነ አባቶቻችን ሊቃነ ጳጳሳት ምዕመናንን ከመባረክ፣ የሚነበቡ ሕያዋን መጻሕፍ ናቸውና በኑሮአቸው ከማስተማርም አልፈው ተቀድተው ከማያልቀው ዕውቀታቸው ደካሞችን የምያበረቱበትን ድርሳናት ቢደርልን ምኞታችን ነው፡፡ በተለይ ከቁጥራቸው ማነስና ከምዕመናን ብዛት አንጻር በአካል አግኝተው ትምህርታቸውን ለመከታተል ለማይችሉት እንዲሁም አረፍተ ዘመን ከገታቸው በኋላ ለሚመጣው ትውልድ ሕያው ትምህርት አበርክተው ቢያልፉ ምንኛ ደስ ባለን ነበር፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እስካሁን ስድስት ያህል ፓትርያርኮችን የሾመት ቢሆንም ከሌሎች አቢያተ ክርስቲያናት አባቶች አንጻር እነዚህ አባቶች ያበረከቱት ድርሳናት እና መጻሕፍት እዚህ ግባ የሚባሉ አይደሉም፡፡ ለአብነት ያህል በአርባ ዓመት ዘመነ ፕትርክናቸው ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ ካበረከቱት ለቁጥር ከሚታክቱ መጻሕፍት አንጻር ሃያ አመታትን በመንበሩ በተቀመጡት በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የተደረሰ ያነበብኩትን አንድም መጽሐፍ አላስታውስም፡፡ በእርግጥ የቀድሞዎቹን ባላውቅም አሁን ያሉት ሌሎች ኤጲስቆጶሳነትን ጨምሮ ብዙዎቹ የእኛ አባቶች የአስተዳደር ሥራ ላይ ብዙ ትኩረት የሚደርጉ ሆነዋል፡፡ እንዲያውም ፓትርያርኮቹማ ደብዳቤ መጻፍና መግለጫ መስጠትን ዋና ሥራቸው ያደረጉ ይመስላሉ፡፡ ነገር ግን ጌታ በመጨረሻ ሲመጣ እኛን ምዕመናንን ስንት መግለጫቸውን እንደሰማን፣ ስንት ደብዳቤአቸውን እንዳነበብን ወዘተ እንደማይጠይቀንና ዋጋ እንደማይሰጠን ሁሉ እኒህ አባቶቻችንም በዚህ ድርጊታቸው አይመዘኑም፡፡ ይልቁንም መንጋውን ምን ያህል ከመናፍቃንና ከቀሳጥያን እንዲሁም ከዘመኑ አላውያን ጠብቃችኋል? ምን ያህልስ የሕይወት ምግብ መግባትኋቸዋል? ተብለው መጠየቃቸው አይቀርም፡፡ ለሁሉም ቸሩ እግዚአብሔር ይህን መልካም ምኞታችንን እንዲሰጠን አጥብቀን ልንለምነው ይገባል፡፡
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

·         ጳጳሳት የፓትርያርኩን የማኅበረ ቅዱሳን ደንብ ማሻሻያ ቅድመ ኹኔታ አልተቀበሉትም::

·         ‹‹ቅድመ ኹኔታው የማኅበሩን አገልግሎት የሚያቀጭጭና በሒደትም የሚያስቆም ነው›› /ታዛቢዎች/

(አዲስ አድማስ ጋዜጣ):- የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅን እንደ አንድ አጀንዳ የያዘው የዘንድሮው የሲኖዶሱ የርክበ ካህናት ጉባኤ ከረቂቁ ጋር በተያያዘ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል በተፈጠረ ፍጥጫ መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡ የፍጥጫው መንሥኤ፣ በቅዱስ ሲኖዶሱ የተሠየመው የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደርያ ደንብ አጥኚ ኮሚቴ ያዘጋጀው የማሻሻያ ረቂቅ በዝርዝር ከመታየቱ አስቀድሞ ፓትርያርኩ ለውይይቱ እንደ ቅድመ ኹኔታ ያቀረቧቸው ነጥቦች በአብዛኛው የጉባኤው አባላት የገጠመው ተቃውሞ እንደኾነ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

የቅ/ሲኖዶሱን ስብሰባ በርእሰ ጉባኤነት የሚመሩት ፓትርያርኩ፤ በአጀንዳው ላይ የሚካሔደውን ውይይት ቀጣይነት ይወስናል በሚል ካቀረቧቸው ቅድመ ኹኔታዎች ውስጥ÷ ለአጥኚ ኮሚቴው መመሪያ የሰጡባቸው ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› አንድም ሳይቀነሱ በደንቡ እንዲካተቱና ረቂቁ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ከጸደቀ በኋላ እንዲታይ የሚሉ እንደሚገኙበት ተመልክቷል፡፡
ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ አስቀምጠዋቸዋል በተባሉት ነጥቦች ስምምነት ላይ ከተደረሰ ስብሰባው ሊቀጥል እንደሚችል በመጥቀስ፣ ኃይለ ቃልም ተማኅፅኖም በተቀላቀለበት አኳኋን መጠየቃቸው ተዘግቧል፡፡
ይኹንና የሚበዙት ሊቃነ ጳጳሳት በቀጥታ እንደተቃወሟቸው፣ የተቀሩትም ድጋፍ ከመስጠት እንደተቆጠቡ ታውቋል፡፡ ፍጥጫው ቀጥሎ አቡነ ማትያስ ‹‹አቋሜ ይኽው ነው፤›› በሚል አጀንዳውን መዝጋታቸውን ሲያስታውቁም፣ ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ እንዲህ ተብሎ የሚተው አይደለም፤›› በሚል ከኹሉም ሊቃነ ጳጳሳት ጠንካራ ተቃውሞ እንደገጠማቸው ምንጮች ይገልፃሉ፡፡
የቅ/ሲኖዶሱ መደበኛ ስብሰባ የሚካሔደው ምልዓተ ጉባኤው ከጅምሩ ተስማምቶ ባጸደቃቸው የመነጋገርያ አጀንዳዎች መሠረት እንደኾነ በሊቃነ ጳጳሳቱ ተቃውሞ ተጠቅሷል፡፡
የማኅበሩ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ እንዲቀርብ ከታዘዘበት ከጥቅምት2005 .. ጀምሮ እየተንከባለለ ለኹለት ዓመታት መዘግየቱን ሊቃነ ጳጳሳቱ አስታውሰው፣ የተጓተተው አጀንዳ ‹‹የማኅበሩን አገልግሎት ያቀጭጫሉ፣ በሒደትም ያስቆማሉ›› በሚል በተተቹት የፓትርያርኩ ቅድመ ኹኔታዎች ሊዘጋ እንደማይችልና ተጨማሪ ጊዜ ሳይወስድ /ሲኖዶሱ ሊወያይበት እንደሚገባ በአጽንዖት በመናገራቸው፣ ጉዳዩ ሳይቋጭ ለቀጣዩ ቀን በይደር ተላልፏል፡፡
አጀንዳው ሰኞ፣ ግንቦት 18 ቀን2006 .. ጥዋት መታየት ሲጀምር፣ አጥኚ ኮሚቴው 37 አንቀጾችና 34 ገጾች አሻሽሎ ያዘጋጀው የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብና የኮሚቴው ቃለ ጉባኤ በንባብ መሰማቱም ታውቋል፡፡ ፓትርያርኩ ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› በሚል ራሱን በቻለ ርእስ በደንቡ እንዲካተት ለአጥኚ ኮሚቴው ጥብቅ መመሪያ የሰጡበት ባለ24 አንቀጽ ሰነድም አብሮ እንዲነበብላቸው መጠየቃቸው የመጀመሪያው ቀን የፍጥጫ መነሻ እንደነበር ታውቋል፡፡
24 አንቀጾችና በአምስት ገጾች የተዘረዘሩት የፓትርያርኩ ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች÷ በአባላቱ በጎ ፈቃድ ተቋቁሞ ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ የሚገኘውን ማኅበር፤ ከሕገ ተፈጥሮው ውጭ የሚያደርግ፣ በቅ/ሲኖዶሱ ፈቃድ ከሚመራበት ደንብ በተፃራሪ ተቋማዊ ህልውናውን፣ የአመራር ምርጫውን፣ የአባላት አያያዙንና የሥራ ቦታውን ለውጭ ተጽዕኖ አሳልፎ የሚሰጥና አጣብቂኝ ውስጥ የሚያስገባ፣ በአርኣያነት የሚጠቀሰውን የፋይናንስ አሠራሩን ወደ ኋላ የሚጎትት መኾኑን እንደተረዱ ያብራሩ አንድ የቅ/ሲኖዶሱ አባል፣ ‹‹ቀጣዩ ቀንም የከበደ ነገር ይዞ እንደሚመጣ ግልጽ ነበር፤›› ይላሉ፡፡
በይደር የተያዘው አጀንዳ በቀጣዩ ቀን ማክሰኞ ጥዋት ተጀምሮ ለግማሽ ቀን የቀጠለ ቢኾንም ፓትርያርኩና ሊቃነ ጳጳሳቱ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያውን በዝርዝር ለመመልከት የሚያስችል ስምምነት ላይ ለመድረስ እንዳልቻሉ ታውቋል፡፡
‹‹ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ ያስቀመጧቸውን ነጥቦችና በአጀንዳው ቀጣይነት ላይ የያዙትን አቋም አልቀየሩም፤ ሊቃነ ጳጳሳቱም ባጸደቅነው አጀንዳ መሠረት ቅድሚያ ሰጥተን መነጋገር ያለብን የሠየምነው አጥኚ ኮሚቴ አዘጋጅቶ ባቀረበው ረቂቅ ላይ ነው፤ መካተት ያለበት ነገር ካለም ማኅበሩን በሚያሠራ መልኩ እያገናዘብን በሒደት እናየዋለን እንጂ አጀንዳው በቅድመ ኹኔታ መታሰር የለበትም በሚል ለማስረዳት ጣሩ፤ በመጨረሻም ፓትርያርኩእንግዲያውስ ስብሰባውን ለመምራት አልችልምበማለታቸው የስብሰባው መቋጫ ኾኗል፤›› ይላሉሒደቱን ለአዲስ አድማስ የገለጹ የስብሰባው ምንጮች፡፡
የማኅበሩ ደንብ በመጀመሪያ ረድፍ ከሰፈሩት የቅ/ሲኖዶሱ መነጋገርያ ነጥቦች አንዱ እንደነበር ያስተዋሉ ሌሎች የስብሰባው ተከታታዮች በበኩላቸው፤ አጀንዳው ከቅደም ተከተሉ ወጥቶ እየተገፋ በመጨረሻ መነሣቱ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል ይህ ዓይነቱ አለመግባባት ሊነሣ እንደሚችል ጠቋሚ ነበር ብለዋል፡፡ 
ተከታታዮቹ አክለውም፣ ፓትርያርኩ ስብሰባውን ለመምራት ፈቃደኛ ባይኾኑም በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በተደነገገው የቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ ሥነ ሥርዓት መሠረት፣ ምልዓተ ጉባኤው በማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያዎች ላይ የጀመረውን ውይይት ቀጥሎ ውሳኔ ለማሳለፍ የሚችልባቸው አግባቦች እንደነበሩ ገልጸው፣ /ሲኖዶሱ በግለጫው የመጨረሻው አጀንዳው ባደረገው የማኅበሩ ደንብ ላይውይይት ተደርጎበታልከማለት በስተቀር ስብሰባውን የቋጨበት አኳኋን ያልተለመደና አደናጋሪ ነው ብለዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን የዘመኑን ኦርቶዶክሳዊ ትውልድ አደራጅቶ ማንነቱን የሚያውቅበትንና በግብረ ገብ የሚታነፅበትን ትምህርተ ሃይማኖት ከማስተማር ባሻገር፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማት አገልግሎታቸውን በብቃት የሚወጡበትን ኹለገብ ሞያዊ ድጋፍ የመስጠት ሓላፊነት እንዳለበት በደንብ አጥኚ ኮሚቴው ማሻሻያ ረቂቅ ላይ መስፈሩ ታውቋል፡፡
ይኹንና ‹‹ጥበቃና ጥንቃቄ›› በሚል ፓትርያርኩ እንደ መመሪያ ያቀረቧቸው ድንጋጌዎችና ግዴታዎች እንዲሁም ከልዩ /ቤታቸው ማኅበሩን አስመልክቶ በየጊዜው የሚወጡ መመሪያዎች የማኅበሩን አገልግሎት የማቀጨጭ፣ በሒደትም አዳክሞ የማስቆም ውጤት ሊኖራቸው እንደሚችል ታዛቢዎች ያስረዳሉ፡፡
የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ፣ /ሲኖዶሱ የማኅበሩ ደንብ እንዲሻሻል ግንቦት 14 ቀን2004 .. ባካሔደው ስብሰባ÷ ማኅበሩ ከጊዜው ጋር የሚሔድ፣ አገልግሎቱና አደረጃጀቱ የደረሰበትን ስፋትና ዕድገት የሚመጥን፣ ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ ልማት የሚጠቅም ድርጅታዊ መዋቅር እንደሚያስፈልገው ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት አምስት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ገለልተኛ የሕግ ባለሞያዎችና የማኅበሩ አባላት በታከሉበት አጥኚ ኮሚቴ የጋራ ጥናት የተዘጋጀ መኾኑ ተመልክቷል፡፡
በግንቦት ወር1984 .. በበጎ ፈቃድ በተሰበሰቡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተመሠረተው ማኅበሩ፤ እየተመራ ያለው /ሲኖዶስ 1994 .. ለሦስተኛ ጊዜ አሻሽሎ በሰጠው መተዳደርያ ደንብ ሲኾን አሁን የተሻሻለው ረቂቅ ተመርምሮ ባለመጽደቁ በነባሩ ደንብ እየተመራ ለመቀጠል እንደሚገደድ ተመልክቷል፡፡
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(መሪጌታ ዘድንግል ለደጀ-ሰላም እንደጻፉት/ PDF)
ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ “አሜሃ ይከውን ኃዘን ዘኢይበቊዕ ኃዘን = ያን ጊዜ ኃዘን ይሆናል ግን የማይጠቅም ኃዘን ነው” እንዳለ የማይጠቅም ኃዘን የሚያዝኑ ብዙዎች ናቸው። ከነዚያው ዘንድ ቅሉ ይሁዳ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ነው። ይሁዳ በፈጸመው እኩይ ግብር ኃዘን በተሰማው ጊዜ የሄደው ወደ ካህናቱ አለቆችና ወደ ሕዝቡ ሽማግሎች ነበር። በደሉንም መናዘዝ የጀመረው በደልን ፀነሰው፣ ወልደውና አሳድገው ለመዓርገ ሞተ ነፍስ ላደረሱና ላበቁ ፈሪሳውያን ነበር። በማቴዎስ 23፥15  “አንድ ሰው ልታሳምኑ በባሕርና በደረቅ ስለምትዞሩ፣ በሆነም ጊዜ ከእናንተ ይልቅ ሁለት እጥፍ የባሰ የገሃነም ልጅ ስለምታደርጉት ወዮላችሁ” ተብሎ እንደተጻፈ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ይሁዳን በክፉ ግብራቸው አጥምቀው የነሱ ፈጻሜ ፈቃድ/ፈቃድ ፈጻሚ ለማድረግ ብዙ ደክመዋል። ጨርሶ የድኅነት በር እንዳይከፈትለት አድርገው ለገሃነም ዳርገውታል። “ከጥፋት ልጅ በቀር ከእነርሱ ማንም አልጠፋም” እንዳለ ወንጌለ ዮሐንስ። (ዮሐ 16፥12)

ወደ እነዚህ ሰዎች ዘንድ ሄዶ ነው ይሁዳ ብሶቱን ለመግለጽ የሞከረው። የብዙ ጊዜ ሕልማችን ግቡን የመታው በዚህ ሰው ተሳትፎና ትብብር ነው ብለው ጊዜ ሰጥተው ሊያነጋግሩትና ሊያጽናኑት ፈቃደኞች አልነበሩም። እነሱ  ምን ገዷቸው። ቢገዳቸውማ ንጹሕ እንዲፈስ ደሙ በእኛ በልጆቻችን ላይ ይሁን ብለው ይምሉ ነበርን? እነሱስ ይሁን ወደው በፈጸሙት ነው። ልጆቻቸው ምን አደረጉ? ረ ወዲያ እነሱ ምን ገዷቸው።
ዛሬም ይህንኑ ታሪክ በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደገሙ ያሉ ሰዎች አሉ። እነዚህ በአየርም በመሬትም፣ በየብስም በባሕርም፣ በአራቱ ማዕዘን ሁሉ ይዞራሉ። ዓላማቸውም የሚቻል ከሆነ ቤተ ክርስቲያንን ከመሠረቷ አፈራርሶ መጣልና ትውልዱ የሚረከበው ሐዋርያዊ ትምህርተ ሃይማኖትና ቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንዳይኖር ማድረግ ነው። ይህን በማድረጋቸው ምን ይጠቀማሉ ቢሉ? ምን ገዷቸው የሚል ነው መልሱ። ቤተ ክርስቲያኒቱ ልብስ ጉርስ ሰጥታ፣ ጉባኤ ዘርግታ፣ መምህር መድባ፣ የአገልግሎት መድረክ ሰጥታ ለቁም ነገር ካበቃቻቸው በኋላ “ዘይሴሰይ እክልየ አንሥአ ሰኰናሁ ላዕሌየ፤ እህሌን የተመገበ ሰኰናውን በኔ ላይ አነሣ” እንዳለ ነቢዩ በሌሊት ከቤተ ጉባኤ እየወጡ ቤተ ክርስቲያን ሞታ የምትቀበርበትን ጉድጓድ ሲቆፍሩ ያድራሉ። በውስጣቸው ነጣቂ ተኵላዎች ሆነው ሳለ የበግ ለምድ ለብሰው ከእውነተኞቹ አገልጋዮች ጋር ተሰልፈው ይቆማሉ። እንኳን እግዚአብሔር እኛም አውቀናቸዋል። እስከ መከር አብረው ይደጉ የሚል አምላካዊ ቃል ስላለ የመከሩን ዘመን እየጠበቅን ነው እንጂ። ወይ ግሩም! መከሩማ ዕለተ ምጽአት አይደለምን የሚል ቢኖር አዎ እርግጥ ነው ግን እግዚአብሔር ሰይፈ በቀሉን በመናፍቃን ላይ የሚያነሣበት ጊዜ ሁሉ መከር ነው ብለን እንመልሳለን።  ጉባኤ ኒቂያ፣ ጉባኤ ቁስጥንጥንያ፣ ጉባኤ ኤፌሶን የመከር ወቅቶች ነበሩና። ከስንዴው ጋር አብረው አድገው የነበሩ እንክርዳዶች በጥብዓተ ሃይማኖትና በነገረ ሃይማኖት ማጭድ እየታጨዱ በቃለ ግዘት ታስረው ወደማይጠፋው እሳት ተጥለዋልና።
ፈሪሳውያን ከቤተ መቅደስ እንዲወጣ ያደረጉት በይሁዳ እጅ ላይ የነበረውን ሠላሳ ብር ነው። (የሰጡት እነሱ መሆናቸው ሳይዘነጋ) የዛሬዎቹ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ግን እነሱ ከሚሞነጫጭሯቸው ምኑናት/የተናቁና የተዋረዱ መጣጥፎቻቸው በቀር ምንም አይነት ነገር በቤተ ክርስቲያን እንዲኖር አይፈልጉም።
እስቲ ከሞነጫጨሯቸው አንዱን እናንሣ።  «ፋሲካችን ማነው? ክርስቶስ ወይስ ማርያም» የሚለውን ጥያቄ በማንሣት በበዓለ ሃምሳ ቅድመ ጸሎተ ኪዳን የሚደርሰውን «ለአዳም ፋሲካሁ፤ የአዳም ፋሲካ» የሚለውን የምስጋና ክፍል ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ ድርሰት ነው በማለት ካህናቱ ምሥጢሩን ሳይረዱ፣ ምን ያህል ስህተት እንደሆነ ሳይገነዘቡ በልማድ በዜማ ስለሚሉት የዚህ ድርሰት ችግር ሳይታያቸው ያለምንም ቅሬታና መሳቀቅ አፋቸውን ሞልተው ያዜሙታል እያሉ የድንቁርናቸውን ጣሪያ ያሳዩናል። ምን ገዷቸው።  «ልጅ ለናቷ…» አይደል የተባለው።
ካህናቱ የዚህ ኃይለ ቃል ምሥጢር ካልገባቸው እነሱን ከሰማይ መልአክ ወርዶ አስተምሯቸው ነው? ወይስ እነርሱ ራሳቸው ከሰማይ ወርደው ይሆን? ይህ ሥርዓት የሚከናወነው በአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ብቻ ቢሆን ጥያቄያቸው ለውይይት በቀረበ ነበር። ነገር ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለችበትና ካህናቶቿና ምእመናኖቿ ባሉበት የሚከናወን ልዩ ሥርዓተ ጸሎት ነው።  አስተውሉ!  «ካህናቱ» የሚለው ቃል ከላይ እስከታች ያሉ አገልጋዮችን የሚወክል ቃል ነው። እንዳው በኔ ሞት አላዋቂ ማነው? መልሱን ለአንባቢ።
ፋሲካ ማለት ምን ማለት ነው?
1· እግዚአብሔር ለሙሴ እንዲህ ብሎት ነበር። «ትበልዕዎ በጒጒዓ እስመ ፋሲካሁ ለእግዚአብሔር = የእግዚአብሔር ፋሲካ ነውና በፍጥነት ትመገቡታላችሁ» ዘጸ 12፥11፤  የእግዚአብሔር ፋሲካ የተባለው እስራኤል በቤታቸው የሠዉት በግዓ ፋሲካ ነው።
ዕዝራም «በሙሴ መጽሐፍ እንደተጻፈው በኢየሩሳሌም ባለው በእግዚአብሔር አገልግሎት ላይ ካህናቱን በየማዕርጋቸው ሌዋውያኑንም በየክፍላቸው አቆሙ ምርኮኞቹም በመጀመሪያው ወር በአሥራ አራተኛው ቀን ፋሲካውን አደረጉ ካህናቱና ሌዋውያኑም አንድ ሆነው ነጽተው ነበር። ሁሉም ንጹሐን ነበሩ ለምርኮኞቹም ሁሉ፣ ለወንድሞቻቸውም ለካህናቱ፣ ለራሳቸውም ፋሲካውን አረዱ» ብሏል። ዕዝራ 6፥18-20፤
ስለዚህ በዚህ ክፍለ ንባብ መሠረት ፋሲካ ማለት አንደኛ፦ በዓልን የሚያመለክት ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ ለበዓሉ የሚቀርበውን መሥዋዕት ያመለክታል።
2· ደስታ ማለት ነው። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ «ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ = ምድር በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካን ታደርጋለች» ብሎ ዘምሯልና። የዚህ ክፍለ ንባብ ምንጭ «ይትፌሣሕ ሰማይ ወትትሐሠይ ምድር = ሰማይ ደስ ይለዋል ምድርም ደስ ይላታል» የሚል ነው። ሥረወ ቃሉም የሚገኘው በኢሳይያስ 44፥23 ላይ ነው። ስለዚህ ፋሲካ ማለት ደስታ ማለት ነው።
3· ማዕዶት ወይም መሻገሪያ ማለት ነው።  «ፋሲካ ብሂል ማዕዶት ብሂል በዘቦቱ ዓዶነ እሞት ውስተ ሕይወት = ፋሲካ ማለት ከሞት ወደ ሕይወት የተሻገርንበት ማዕዶት ማለት ነው» ብሎ እንደዘመረ ቅዱስ ያሬድ።
4· ቀዳማዊ ሕግ ማለት ነው። «ዛቲ ፋሲካ ቀዳሚት ሕግ = ይህች ፋሲካ የሕግ መጀመሪያ ናት» እንዲል።
5· የትንሣኤው መታሰቢያ ነው። «ፋሲካ ፋሲካ ፋሲካ ተዝካረ ትንሣኤሁ ለመድኃኒነ = ፋሲካ የመድኃኒታችን የትንሣኤው መታሰቢያ ናት» እንዲል።
6· ትንሣኤ ማለት ነው። «ትንሣኤ ሰመያ ለበዓለ ፋሲካ = የፋሲካ በዓልን ትንሣኤ ብሎ ሠየማት» እንዲል። ትንሣኤም ሁለት አይነት ነው። ትንሣኤ ልቡናና ትንሣኤ ዘጉባኤ።
በውኑ መንፈሳዊ እረፍትና ደስታ ለማግኘታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደእኛ ለመምጣቱ ምክንያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አይደለችምን? ፀረ ማርያም አቋም ያላቸውና ነዳያነ አእምሮ የሆኑ ይህ አይዋጥላቸውም ይሆናል። ለነገሩ ምን ገዷቸው።
ከላይ ፋሲካ ማለት ቀዳማዊ ሕግ ማለት ነው ማለታችን ይታወሳል። የመጀመሪያውን ቃለ ብሥራት በመስማት እመቤታችን ዓለሙ በኃዘን እንዳይጠፋ «ይኩነኒ = ይደረግልኝ» በማለት ቀዳማዊት አይደለችምን። ከሷ ተወልዶ ዓለሙን ከወደቀበት መርገም እንደሚያድነው ሲነግራት እራሷን አሳልፋ አልሰጠችምን? ከዚህ በላይ ፋሲካ መሆንና መባል ከወዴት አለ? ልጇን እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስን ራሱን ለመስቀል አሳልፎ በመስጠቱ ፋሲካችን ስንለው እሷንም  ለእግዚብሔር ፈቃድና ዓላማ ለእኛም የዘለዓለም ሕይወት ምክንያተ ድኅነት ለመሆን ራሷን አሳልፋ ስለሰጠች የአዳም ፋሲካ እንላታለን።
ሌላው ይህን ክፍለ ጸሎት ለመንቀፍ የተዘጋጁ ሰዎች የራሳቸው የሆነ ችግር አለባቸው።  የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል፦
1፣ ይህ ጸሎት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚጸለው በቃል ነው። በቃል ለማጥናት ደግሞ ትጋትና ማስታወስ አስፈላጊ ነው።  እነዚህ ሰዎች ሙሉ ጊዜያቸውን የሚያውሉት ለከንቱ ወሬና ለከርሣቸው የሚሆን ፍርፋሪ ለመፈለግ ስለሆነ አይሆንላቸውም። ከሊቃውንቱ ጋር አብረው ቆመው መጽሐፍ ዘርገተው ቢታዩ ደግሞ ውርደት ይመስላቸዋል። እነዕገሌ ሁሉ በቃላቸው ነው ምነው እናንተስ ከሚለው ጥያቄ መሸሽ ይፈልጋሉ።  ከማን አንሼ አይነት ነገር ይመስላል።
2፣ የአገልግሎት ፍቅርና መንፈስ ጨርሶ የላቸውም። እንቅልፋሞችም ናቸው። ተርእዮ ይወዳሉ። ሰው በሚበዛበት ጊዜና መድረክ እንጂ መገኘት የሚፈልጉት በተመስጦ ሆኖ ወደ እግዚአብሔር በሚቀርብ አገልግሎት መገኘት አይወዱም። ማን ሊያያቸው። ቀድማችሁ ገብታችሁ አገልግሉ እንዳይባሉ አገልግሎቱን ማጥላላት ምርጫቸው ሆነ።
3፣ እኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት አይመቻቸውም። ለምሳሌ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ ወማዕዶታ ለሔዋን እንተ ይእቲ ዓፅመ ገቦሁ» የሚለውን ሲጠቅሱ «እስመ ግእዛኖሙ ኮነ ለወልድኪ በትንሣኤሁ = በልጅሽ ትንሣኤ ነፃነታቸው ተደርጓልና» የሚለውን መጥቀስ አይፈልጉም። በትርጓሜያችን መጽሐፍ ጭብጡን አይለቅም  ለሸፋጭ ለለዋጭ አይመችም የሚል ሐተታ አለ። ለሸፍጣቸው ስለማይመቻቸው ለማጥፋት የቻሉትን ያህል ይደክማሉ።
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ፋሲካ» የተባለው በለበሰው ሥጋ ነው። ይህም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ «ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘየአትት ኃጢአተ ዓለም = የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ እነሆ» በማለት የተናገረውን የሚተረጉም ነው። ቅዱሳት መጻሕፍት እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስን «በግ» እያሉ  ሲገልጹት እሱ ራሱ በርሱ ያመኑ ምእመናን «በጎች» በማለት ይጠራቸዋል።  ይህ ማለት የምእመናን «አባግዕ» መባልና መሆን የክርስቶስን ስፍራ ይይዛል ወይም ይተካል ማለት አይደለም።  ለዚህ ነው ሊቁ «ለአዳም ፋሲካሁ» ካለ በኋላ «እስመ ግእዛኖሙ ኮነ ለወልድኪ በትንሣኤሁ = በልጅሽ ትንሣኤ ነፃነታቸው ተደርጓልና» በማለት ማስረጃ ያስቀመጠው።
ቅዱስ ኤፍሬምም በቀዳሚት ውዳሴው «ትትፌሣሕ ገነት እመ በግዕ ነባቢ ወልደ አብ ዘይነብር ለዓለም = ለዘለዓለም ጸንቶ የሚኖር የአብ ልጅ የተናጋሪው በግ እናት ገነት/እመቤታችን ደስ ትሰኛለች» ብሏል። እናቱ ስትደሰት የማይደሰት ልጅ የለምና።    «ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ» ብሎ የገባለትን ቃል የፈጸመለት ከእመቤታችን ሰው በመሆን ነውና። እባብ የሞቱ ምክንያት እንደሆነ ሁሉ እመቤታችንም የድኅነቱና የፋሲካው ምክንያት ናትና።
ሊቃውንት በየድርሳናቸው «ትምክሕተ ኵልነ፣ አንቲ በአማን ምክሐ ዘመድነ፣ ትክምሕተ ዘመድነ በወሊዶተ ዚአከ = የሁላችን መመኪያ፣ አንቲ የባሕርያቺን መመኪያ ነሽ፣ አንተን በመውለዷ የባሕርያችን መመኪያ ናት» እያሉ የገለጿት የአዳም ፋሲካ/ደስታ በመሆኗ ነው። እግዚአብሔር ከሰማይ ወደምድር በተመለከተ ጊዜ እሱን የሚፈልግ ጠቢብ ሰው አለማግኘቱን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ። መዝ 13፥2፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ለአዳም የገባው ቃል ኪዳን የሚፈጸምበት ዘመን ሲደርስ መልአኩን ልኮታል። «ወበሳድስ ወርኅ ተፈነወ ገብርኤል መልአክ እምኀበ እግዚአብሔር = በስድስተኛው ወር መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ» እንዳለ ወንጌለ ሉቃስ። ሲያበሥራትም «ተፈሥሒ ፍሥሕት ኦ ምልዕተ ጸጋ እግዚአብሔር ምስሌኪ = ደስ የተሰኘሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነውና ደስ ይበልሽ» በማለት ነው።  ስለዚህም ድንግል ማርያም የአዳም ፋሲካ/ደስታ ናት።
ቅዱስ መጽሐፍ ሔዋንን «የሕያዋን ሁሉ እናት» (ዘፍ 3፥20) ብሎ ሲጠራት እመ ሕይወት ድንግል ማርያምን ፋሲካ ብንላት አላዋቂነት ነውን?
ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣመጋቢት/፳፻፪ .):- ሰሙነ ሕማማት የጾመ ሁዳዴ የመጨረሻው ሳምንት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማም የሚታሰብበት ፤ካህናትና ምእመናን በአጸደ ቤተክርስቲያን ተሰብስበው የሕማሙን ነገር የሚያወሳውን ዜማ የሚያዜሙበት፤ግብረ ሕማም በመባል የሚታወቀውን መጽፍ የሚያነቡበትና የሚሰሙበት፤ በነግህ፣ በሠልስት፣ በስድስት፣ በተሰዓት /ዘጠኝ /ሰዓት በሰርክ /በዐስራ አንድ/ ሰዓት እየመላለሱ የሚሰግዱበትና የሚጸለዩበት ልዩ ሳምንት ነውከሆሳዕና ማግስት እስከ ትንሳኤ

በዚህ ሳምንት በተለይ ካህናት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ:: ምክንያቱም ጌታችን የደረሰበትን መከራና ስቃይ እንዲሁም የሰው ልጅ ፭መቶ ዘመን በጨለማ ግዞት ይኖር እንደነበር ለማዘከርም ጭምር ነው። የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራና ሕማም በጽኑ እንድናስበው ያስተማሩን ሐዋርያት ናቸው ለእነርሱም የነገራቸው ደግሞ ራሱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሰሙነ ሕማማት የጌታችንን ሕማማት ከማሰብ ጋር በርካታ ድርጊቶች መፈጸማቸውን የምናስታውስበት ሳምንት ነው::
ሰኞ —- መርገመ በለስ የተፈጸመበት ሰኞ በዚህ ዕለት ጌታችን ከቢታኒያ ሲወጣ ተራበ ቅጠል ያለባትን በለስ ተመልክቶ ወደ በለሲቱ ቢቀርብ ከቅጠል በቀር ምንም ነገር ባለማግኘቱከአሁን ጀምሮ ለዘላለም ምንም ካንቺ ፍሬ አይበላማር ፲፩፥፲፬ በማለት ስለረገማት መርገመ በለስ የተፈጸመበት ሰኞ ይባላል። ይህ ቀን አንጽሖተ ቤተመቅደስ የፈጸመበት ሰኞም ይባላል ።ጌታ ወደ ቤተመቅደስ ሄዶ በቤተመቅደሱ የሚሸጡትን እና የሚለውጡትንቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለችማቴ ፳፩፥፲፫ በማለት ከቤተመቅደስ ገርፎ አስወጥቷቸዋልና።
ማክሰኞ —- የጥያቄ ቀን ሰኞ ዕለት በቤተመቅደስ ሲሸጡ እና ሲለውጡ የነበሩትን ሁሉ እየገረፈ በማባረሩ ምክንያት ለሰው ልጅ ሹመትንና ስልጣንን የሰጠ ጌታበምን ስልጣን ይህንን ታደርጋለህ ?”ማቴ ፳፩፥ ፳፫ ተብሎ በፈሪሳውያን ተጠይቋልና የጥያቄ ቀን ይባላል። በዚህ ዕለት በቤተመቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረም የትምህርት ቀን ይባላል። ሉቃ ፳፩ ፥፳፰ ማር ፲፪፥፪
ረቡዕ —- ምክረ አይሁድ ረቡዕ እለት የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው የመከሩበትና ውሳኔ ያሳለፉበት ቀን በመሆኑ ምክረ አይሁድ ይባላል ።ወቅቱ የፋሲካን በዓል የሚያከብሩበት ቀን በመሆኑ እና ብዙ ህዝብም ጌታን ይከተለው ስለነበር ሁከት እንዳይነሳ ስጋት ነበራቸው ።ነገር ግን ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ አሳልፎ እንደሚሰጣቸው ስለነገራቸው ሉቃ ፳፪፥፩ ጭንቀታቸው ተወግዶ በጌታ መያዝ ተስማምተዋል። የመልካም መዓዛ ቀንም ይባላል።ጌታችን በዚህ ዕለት በለምጻሙ በሰምዖን ቤት ተቀምጦ ሳለ መላ ሕይወቷን ለዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ እፍረት/ባለሽቶዋ ማርያም/ ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ የአልባጥሮስ ሽቱ አምጥታ በራሱ ላይ በማርከፍከፍ ስለቀባቸው ማቴ ፳፮፥፮ የመዓዛ ቀን ይባላል። ይህች ሴት ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት እየለመነች በእግሩ ስር ተደፍታ በእንባዋ እግሩን አርሳለችና ማር ፲፬፥፱ የእንባ ቀን ይባላል።
ሐሙስ —- ጸሎተ ሐሙስ ጌታችን ለአይሁድ ተላልፎ ከመሰጠቱ በፊት በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ ሲጸልይ በማደሩ ማቴ ፳፮፥፴፮ ጸሎተ ሐሙስ ይባላል።ጌታችን የደቀመዛሙርቱን እግር በፍጹም ትህትና ዝቅ ብሎ ያጠበበት ዕለት በመሆኑም ዮሐ ፲፫፥፫፲፩ ሕጽበተ ሐሙስ ይባላል። ከሰባቱ ምስጢራት አንዱ የቅዱስ ቁርባን ምስጢር ማቴ፳፮፥፳፮፳፱ በዚህ ዕለት ተፈጽሟልና የምስጢር ቀን ይባላል። መሥዋዕተ ኦሪት /በእንስሳት ደም የሚቀርብ መሥዋዕት/ቀርቶ ለአለም ድህነት ራሱን ያቀረበበት ቀን በመሆኑ ሉቃ ፳፪፥፳ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል። ለኃጢአትና ለዲያቢሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱን እንዲሁም የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነም ዮሐ ፲፭፥ ፲፭ የነጻነት ሐሙስ ይባላል። 
ዓርብ —- የስቅለት ዓርብ፦ ጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ የዋለበት ዕለት ነውና ማቴ ፳፯፥፴፭ የስቅለት ዓርብ ይባላል። ከጌታ ስቅለት በፊት በተለይም በሮማውያን ህግ የወንጀለኛ መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል ጌታችን በደሙ ቀድሶ የምህረት፣ የሕይወት አርማ የዲያቢሎስ ድል መንሻ ስላደረገው በሞቱ መልካሙን ሕይወት ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ይባላል።
ቅዳሜ —- ቀዳም ስዑር ይህች እለት ከድሮ በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረች ቅዳሜ ታባላለች ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት በመሆኑም ለምለም ቅዳሜ ይባላል ።ምዕመናንም ይህንን ለምለም ቀጤማ እስከ ትንሣኤ ለሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል። ቅዱስ የሆነው እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ያረፈበት ቀን ሲሆን በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ስራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ ሲኦልን በርብሮ ባዶዋን ሲያስቀራት በዚያ የነበሩትን ነፍሳት የዘላለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ቅዱስ ቅዳሜ ያባላል።
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


Source: Courtesy of www.adebabay.com/  PDF

 ይህ ጽሑፍ የእኔን የግል ምልከታና አስተያየት ብቻ የሚመለከት እንጂ በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ስሙ የተጠቀሰውን ማኅበርም ሆነ ከእርሱ ጋር የአገልግሎት ግንኙነት ያላቸውን ተቋማት የማይመለከት መሆኑን አበክሬ በመግለጽ ልጀምር።  

  አንድ ብሒል አለ። ውሸትን ደጋግመው ቢናገሩት እንደ እውነት የሚቀበለው ሰው መፍጠር ይቻላል። ስለዚህም ሐሰተኞች ሐሰታቸውን ሳያሰልሱ በተናገሩት መጠን፦ አንደኛ ራሳቸውንም በሐሰታቸው እውነትነት ያሳምናሉ፤ ብሎም ሌሎችን ማሳመን ይችላሉ። ደጋግሞ የመናገር ጥቅሙ ይኼው ነው።

አንዳንድ እውነት የያዙ ሰዎች ደግሞ “እውነት እስከያዝን ድረስ ደጋግሞ መናገር ለምን ይገባል?” ብለው ያቀርባሉ። እውነት አላቸው። ፀሐይ ሲወጣ ጨለማ መሸሹ፣ ሻማ ሲለኮስ ብርሃን መፈንጠቁ ላይቀር “ጨለማን ማውገዝ ምን ጥቅም አለው?” ይላሉ። ይህም እውነት ነው። “ጨለማን ደጋግሞ ከማውገዝ አንድ ሻማ ማብራት” እንደተባለው። ነገር ግን ሐሰት ተደጋግማ በመነገሯ ተከታይ መፍጠር እስከቻለች ድረስ እውነትን ደጋግሞ በመናገር የሚመጣ ምን ችግር አለ? ሻማውንም እየለኮሱ እውነቱንም ደጋግሞ መናገሩስ? ስለዚህ በእውነት ተደጋግሞ መነገር፣ በሻማ መለኮስም አምናለኹ። ደጊመ ቃል እንዲሉ የኢትዮጵያ ሊቃውንት።

 እንኳን አገር ቤት ያለው አንባቢ ይቅርና እኛ ከአገራችን በብዙ ሺህ ማይሎች ርቀን የምንገኘው ሳንቀር በየዕለቱ የምንኮመኩመው አዲሱ ትኩስ ዜና የማኅበረ ቅዱሳን እና “የተጠመደለት ወጥመድ” ጉዳይ ነው። በማኅበራዊ ድረ ገጾች እና በጡመራ መድረኮች፣ እንዲህ በሕትመት ውጤቶች በሰፊው ሽፋን ያገኘ ጉዳይ ሆኗል። ብዙ ኢትዮጵያውያን (እምነት ሳይለይ) ይህንን ጣልቃ ገብነት በጽኑዕ እየተቃወሙት እያወገዙት ነው። “ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ የሚባል ከሆነ እኔም አክራሪነትን እወደዋለኹ” የሚሉ ሐሳቦች በብዛት ተጽፈው ተመልክቻለኹ።

“የአክራሪነቱ ነገር”፣ ነፍሳቸውን ይማረውና አቶ መለስ በፓርላማ ተናግረውት በነበረ ጊዜ፣ እኔን ጨምሮ ብዙ ፀሐፍት አስተያየታቸውን የሰጡበት ከመሆኑ አንጻር ወደዚያ መመለስ አይገባ ይሆናል። ማኅበሩ ከፓርቲ ፖለቲካ ጋር ግንኙነት እንዳለው በመንግሥት ሰዎች እና በደጋፊዎቻቸው የሚነሣውን ሐሳብ በተመለከተ ግን የግል አስተያየቴን ላሰፍር እወዳለኹ።

ማኅበሩ ፖለቲካ ውስጥ አለበት? ለመሆኑ ፖለቲካ ውስጥ መግባት/ አለመግባት ምንድነው? ማንኛውም ሰው የተባለ ፍጡር ፖለቲካዊ አመለካከት አለው። ፖለቲካ አልወድም የሚሉ ሰዎች ራሳቸው እንኳን ፖለቲካዊ አቋም አላቸው። ልዩነቱ እያወቁ ማወቅ እና ሳያውቁ መኖር ናቸው። የተለያዩ ሐሳቦች እስካሉ ድረስ፣ አስተዳደሮች፣ ገዢዎችና ተገዢዎች እስካለን ድረስ ፖለቲካዊ አመለካከቶች መኖራቸው ግድ ይመስለኛል። “ፖለቲካ እና ኮረንቲ በሩቅ” የሚለው ሰው ራሱ በኮረንቲ ከመጠቀም፣ ሕይወቱ በፖለቲካ ተጽዕኖ ሥር መውደቁ እስካለ ድረስ ፖለቲካ የማይነካው ኢትዮጵያዊ አይኖርም።

ይኼ በፖለቲካ ምሁራን ሳይሆን እኔን በመሳሰሉ ለፖለቲካው ዕውቀት ተርታ በሆንን ሰዎች ቋንቋ “ፖለቲካ ውስጥ መግባት ወይም አለመግባት” የምንለው የፓርቲ ፖለቲካ ውስጥ መግባት ማለታችን እንደሆነ ይሰማኛል። ፖለቲከኞች የምንላቸው እንደዚያ ያሉ ሰዎችን ነውና። ማኅበረ ቅዱሳን “ፖለቲካ ውስጥ ገባ/ አልገባም” የሚለውንም የምፈታው በዚሁ አንድምታውና አገባቡ ብቻ ነው።

ማኅበሩ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ አባላት አሉት። አባላቱ ሰዎች እንደመሆናቸው ፖለቲካዊ አመለካከት አላቸው። ማኅበሩን በአባልነት ለመቀላቀል የሚያበቃቸው ግን ይህ ፖለቲካዊ አመለካከታቸው አይደለም። የአባላቱ የዓላማ አንድነትና መሠረቱ ማኅበሩ የሚያራምደው ቤተ ክርስቲያናዊ አቋም ብቻ ነው። በሃይማኖትና በአገልግሎት ዓላማ አንድ ናቸው እንጂ በፖለቲካ ርዕዮት የተሰባሰቡ አይደሉም። ሲጀመርስ ስለ ፖለቲካ አመለካከታቸው የት ተጠያይቀው? የት ተገማግመው? የት ተለካክተው? በየትኛው ጊዜ?

ስለዚህም ማኅበሩ አንድ ሃይማኖታዊ አቋም ያራምዳል እንጂ “አንድ ፖለቲካዊ አቋም” የሚባል የለውም። ሊኖረውም አይችልም። ለምን? ምክንያቱም “ፖለቲካዊ አቋምን ለማራመድ” መጀመሪያ ፖለቲካዊ አቋም መያዝ ያስፈልገዋል። ያንን ለማድረግ ደግሞ አባላቱን በሙሉ በዚህ ፖለቲካዊ አቋም ማሳመን ያስፈልጋል፤ ያንን ማድረግ ደግሞ አስቸጋሪ ብቻ ሳይሆን ማኅበሩ የያዘውን ሃይማኖታዊ አቋም የሚጻረርና ማንም ሳይነካው እንዲፈርስ የሚያደርገው ድማሚት ነው።

እዚህ ላይ መነሣት ያለበት ቁምነገር፤ የማኅበሩ አባላት በሃይማኖታዊም ሆነ በፖለቲካዊ አስተሳሰባቸው ራሳቸውን የቻሉ (ማለትም ማመዛዘን የሚችሉ) ክርስቲያኖች እንጂ የአንድ ቡድን ጀሌዎች አለመሆናቸውን ነው። ራሱን የቻለ አስተሳሰብ ያለው ማንኛውም ሰው፣ አባል የሚሆንበትን ድርጅት ያያል፤ ይመዝናል፣ ያስባል። እንደማይጠቅመውና እንደማይስማማበት ከተረዳ ይተወዋል። ጀሌ ግን የተነገረውን ተቀብሎ እንደ በቀቀን ያስተጋባል፤ ሳያውቅ አባል ይሆናል፤ በጥቂት ጥቅም ይደለላል፣ የሚኖርለትም-የሚሞትለትም ቋሚ መርሕ አይኖረውም።

ማኅበረ ቅዱሳንን እና አባላቱን በአገራችን ላለፉት 40 ዓመታት በጠነነው የፖለቲካ ድርጅት ጀሌነት መገምገም ትክክል የማይሆነው ለዚህ ነው። አባላቱ አገልጋዮች እንጂ ካድሬዎች አይደሉም። አመራር ላይ የሚቀመጡት ሰዎች በተራቸው ለማገልገል እንጂ ከሌላው አባል የተለየ መርሕ ለማራመድ አይችሉም። እናራምድ ቢሉም አባላቱ ጀሌዎች ስላልሆኑ ሊከተሏቸው የሚችሉበት ምንም መንገድ አይኖርም። የአባላቱ አንድነት በሃይማኖት እና በሃይማኖት ብቻ ነው። በበሰለ ሚዛን የሚለካቸው ቢኖር ኖሮ በዘር፣ በቋንቋ፣ በፖለቲካ አቋም፣ በትምህርት ደረጃ፣ በዕውቀት፣ በዕድሜ ወዘተ ወዘተ የተለያዩ እንጂ እንደ ሜዳ አህያ አንድ ወጥ እና ልሙጥ አለመሆናቸውን ይገነዘባል።

ስለዚህ አንድ አባል በግልጽ አንድ የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ ገብቶ የዜግነት ድርሻውን መወጣት ቢፈልግ ምን ማድረግ እንዳለበት ያውቃል። በማኅበሩ ውስጥ ያለውን የአመራር ኃላፊነት ማስረከብ ይኖርበታል። በዚህ ደረጃ በይፋ ከአመራርነታቸው በሰላም ተሰናብተው ወደፈቀዱት ይፋዊ የፖለቲካ መስመር መጓዝ የቻሉ ሊኖሩ እንደሚችሉ እገምታለሁ። ማኅበሩንም የፖለቲካ ድርጅታቸውንም መምራት የሚችሉበት መንገድ አይኖርም። እነርሱ ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለማቸውን በማኅበሩ ላይ ለመጫን ቢፈልጉም እንኳን “የፍላጎት መላተም” (“conflict of interests”) ስለሚኖር ሊሳካላቸው አይችልም። የማኅበሩ አባላት በፖለቲካ መሳተፍ የዜግነት መብታቸው ሲሆን በማኅበሩ አገልግሎት መሳተፍ ደግሞ ሃይማኖታዊ የትሩፋት ሥራ እንደመሆኑ ማቻቻል የአባሉ ፈንታ ነው።

ማኅበሩ በፖለቲካ ውስጥ ገብቷል የሚለው (በተለይ በቤተ ክህነቱ ዙሪያ ያሉ ሰዎች) ከ1980ዎቹ ጀምሮ ሲያዜሙት የነበረ የሰለቸ ዜማ ነው። የሚነቅፉት ግን ማኅበሩ “ኢሕአዴግን አይደግፍም” ብለው ስላሰቡ እንጂ “ተቃዋሚ ነው ብለው ስላመኑ” ብቻ አይደለም። ለነገሩ እነዚህ መንግሥትን በዱላነት ለመጠቀም የሚፈልጉ፣ በመንፈሳዊም በዓለማዊም ሚዛን ቢመዘኑ ውኃ የማያነሱ ደመናዎች “ፖለቲካ” የሚሉት አጎብዳጅነትን ነው። መንግሥት እነሱን ይጠቀማል። እነሱም በአቅማቸው በመንግሥት ይጠቀማሉ።

ታዲያ ማኅበሩ የትኛውንም የፖለቲካ ድርጅት እንደማይደግፍ ነገሩን ሥራዬ ብሎ ለሚከታተል ለማንኛውም ሰው ግልጽ ሆኖ ሳለ በዚህ ጉዳይ መወንጀሉ ለምን አስፈለገ? ክርስቶስ አምላካችን ራሱ “ግብር አትክፈሉ ይላል? ለቄሳር አትገዙ ብሏል፤ ንጉሣችን ሳይሆን ንጉሥ ነኝ ብሏል” የሚል ፖለቲካዊ ክስ እንደቀረበበት ሃይማኖትን ብለው የሃይማኖት አገልግሎት ላይ የተሠማሩ ሰዎች በየዘመኑ የሚከሰሱበት ጉዳይ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልገናል።

ቅዱስ ሉቃስ “ይህ ሕዝባችንን ሲያጣምም ለቄሣርም ግብር እንዳይሰጥ ሲከለክል ደግሞም፦ እኔ ክርስቶስ ንጉሥ ነኝ ሲል አገኘነው ብለው ይከሱት ጀመር” ሲል እንደጻፈው (ሉቃስ 23፥2)። በሌላው ዓለም ያለውን እንኳን ትተን በአገራችን ያለውን ብናስታውስ፣ ነገር ሰሪዎች በየዘመኑ የነበሩ ቅዱሳን አባቶቻችንን ከነገሥታቱ ጋር በማጋጨት በአደባባይ እስከመገረፍ ያደረሱበት ጊዜ፣ በግዞት በእስር እንዲማቅቁ ያደረጉበት ወቅት እንዳለ ታሪክ ያስተምረናል። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን እና የደብረ ሊባኖስ እጬጌ ጻድቁ አባ ፊሊጶስን ለአብነት ብናንሣ አባ ጊዮርጊስ እንደተጋዘ፣ አባ ፊሊጶስ በአደባባይ ራቁቱን እንደተገረፈ እናነባለን።

ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ አገልግሎት ላይ ያለ ማኅበር ትናንት እንደፈላ እንደ ክረምት አግቢ ሊታይ አይችልም። መንግሥት ይኼ ሁሉ ሐቲት አይጠፋውም። ማኅበሩ ተቃዋሚም ደጋፊም እንዳይደለ መግለጹ እስካሁን ጉንጭ አልፋ ከመሆን አልዘለለም። መደገፍ የማይችል አካል፣ ባይቃወምም እንኳን ገለልተኛ መሆኑ ለአደጋ ያጋልጠናል በሚል “ባልበላውም ጭሬ ላፍሰው” የዶሮ ፍልስፍና የተቃኘ ነው።

ከዚህም ባሻገር አባላቱ ከአንድ ዘርና ቋንቋ፣ ባህልና ፖለቲካዊ አቋም የመጡ አለመሆናቸው፤ ይልቁንም ሕብረ ብሔረሰባዊና ኢትዮጵያዊ መሆናቸው እንቅልፍ የሚነሣቸው አካላት መኖራቸው ግልጽ ነው። “አዳሜ በየቅርጫትህ ግባ” ሲባል አንድ ቅርጫት ውስጥ የማይጨመሩ፣ ከሌላውም ቅርጫት ካለው ጋር ዝምድናና ፍቅር ያላቸው፤ ከቅርጫታቸው ውጪ የሚያስቡ ሰዎች ያሉበት ማኅበር መሆኑ የሚያስፈራቸው አሉ።

በውጪ አገር ባሉ የተለያዩ የመንግሥት ተቃዋሚ ቡድኖች ዘንድ ማኅበረ ቅዱሳን ሲጠረጠር እንደኖረ እነርሱም በፈንታቸው “ማኅበረ ቅዱሳን የኢሕአዴግ ደጋፊ መሆን አለበት” ሲሉ ኖረዋል። ለምን እንዲህ አላችሁ ሲባሉ ምክንያቱም “ይህንን የሚያህል ትልቅ ተቋም እንዴት ነጻና ፍፁም ሃይማኖታዊ ብቻ ሊሆን ይችላል? ጠርጥር ጠርጥር” የሚል ጥርጣሬ ያቀርባሉ።

ማኅበሩ አብሯቸው ጀብ ጀብ ላለማለቱ ምክንያቱ ዓላማውና ተፈጥሮው መሆኑን ለመቀበል የአገር ውስጡም የዳያስጶራውም ቡድን፣ እነዚያም እነዚያም ይኸው እንደተቸገሩ አሉ። እነዚያ “የዚያ ደጋፊ ነው” እንዳሉት፣ እነዚያም “የዚያ ደጋፊ ነው” እንዳሉት። ማኅበሩ ደግሞ “አነ ዘክርስቶስ፣ አነ ዘቤተ ክርስቲያን፤ እኔ የክርስቶስ ነኝ፣ እኔ የቤተ ክርስቲያን ነኝ” እንዳለ አለ። መጨረሻውን ደግሞ ዕድሜ ይስጠን እንጂ፣ እናየዋለን።

     ይቆየን – ያቆየን  
(ኤፍሬም እሸቴ)

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

( አረጋዊለደጀሰላም እንደጻፉት መጋቢት 27/2006 ዓ.ም፤ April 5/2014)፦ ታላቁ የእግዚአብሔር ነቢይ የማይቀረውን የኢየሩሳሌምን ጥፋትና በከላውዴዎን ንጉስ እጅ፣ ለከለዳውያን ሠራዊትና፣ ለባቢሎን ሕዝብ ተላልፋ መሰጠቷን እግዚአብሔር ራሱ በተረዳ ነገር በገለጠለት ጊዜ ነቢዩ ኤርምያስ ልብሱን ቀዶ፣ በራሱም ላይ ትቢያ ነስንሶ፣ በቤተ መቅደስ ውስጥ ከባሮክ ጋር እያለቀሱ ተቀመጡ፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ እግዚአብሔርንም ሁለት ታላቅ ነገሮች ለመነው። ጉዳዮቹም፦  

፩ኛ. ተሰውረው እግዚአብሔርን ስለሚያገለግሉባቸው ንዋያተ ቅድሳት ዕጣ ፈንታ  እና
፪ኛ. ስለ ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ ጉዳይ ነበር፡፡

 

ኤርምያስም እንዲህ ሲል ተናገረ፤ “ ጌታዬ ሆይ፤ እለምንሃለሁ፣ ሕዝቡን ብዙ ዘመን ለጠበቃቸው፣ እኔን ባሪያህ ኤርምያስንም ከሃገሩ ሰው ሁሉ ይልቅ ለጠበቀኝ ለኢትዮጵያዊው ለአቤሜሌክ የማደርገውን ግለጥልኝ፡፡ እርሱ ከረግረግ ጒድጓድ አወጣኝ፣ እንዳያዝን የከተማዋን ጥፋት ያይ ዘንድ አልወድለትም” (ተረፈ ባሮክ ፪፥ ፰-፱)።
ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ በነቢዩ በኤርምያስ እንደተመሰከረለት በዚያ ዘመን ከነበረ ማንኛውም እስራኤላዊ ወይም የኢየሩሳሌም ነዋሪ ይልቅ የከተማዋ ለባዕዳን ወረራ ተላልፋ መሰጠት እና ከዚያም ጋር ተያይዞ የሚመጣውን የጥፋት ዘመን ቢመለከት እጅግ የሚያዝንና በኃዘኑም አብዝቶ የሚጎዳ መሆኑን ነበር፡፡
እንግዲህ ነቢዩ  ኤርምያስ “…. እንዳያዝን የከተማዋን ጥፋት ያይ ዘንድ አልወድለትም” ብሎ እንደማለደለትና የኃያሉ የእግዚአብሔር ቸርነት ተደርጎለት አቤሜሌክ እንደዋዛ ለ66 ዓመታት አንቀላፍቶ የወዳጆቹን የእስራኤላውያንን መከራና ስቃይ እንዲሁም የሚወዳትን የኢየሩሳሌምን በጠላት መወረርና መጥፋቷን ሳያይ ቀርቷል፡፡
አባቶቻችን እንኳንስ ለታላቋ ውድ ሀገራቸው ለኢትዮጵያ አንድነት እና ነጻነት፣ ለቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናቸው ልዕልና እና ክብር ይቅርና በፍቅርና በሰላም ለተወዳጇቸው ሁሉ ከራስ በላይ የሚታመኑ የልብ ወዳጅ የሚሆኑ እና የወዳጆቻቸውን ጥፋት በቸልታ የማይመለከቱ የእውነትና የደግነት አውራ መሆናቸውን በብዙ የተከበሩና የታመኑ የዓለማችን ታሪካዊ መዛግብት ላይ ሰፍሮ እናገኛለን፡፡ ይልቁንም በታላቁ መጽሐፍ፡፡
እውነት ነው! እነዛ ቅዱሳንና ጽኑዓን አባቶቻችን በዘመናቸው ከተነሱባቸው ሀገር አፍራሽ፣ ሃይማኖት ለዋጭና፣ ታሪክ አቆሻሽ የሀገር ውስጥና የባዕዳን ጠላቶች ጋር ተጋድለው፣ ኊልቆ መሣፍርት የሌለው ውድ ሕይወታቸውንና ንብረታቸውን ሰውተው እነሆ ዛሬ እኛ በታላቅ ክብርና ሞገስ የምንኖርባትን ብቸኛዋን የክርስቲያን ደሴት አውርሰውናል።
እነሆ ዛሬ ሌላ እውነትም አለን፤ 
ዛሬ በእኛ ዘመን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በጠና ታማለች፡፡ አዎ የመናፍቃንና የኢአማንያን የተቀናጀና የተቀነባበረ የጥቃት ዘመቻ ተከፍቶባታል፡፡ የማይተባበሩት ተባብረውባት፣ አንድ የማይሆኑት በአንድነት ዘምተውባት፣ በቤቷ የተሰገሰጉት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን ከዘመኑ አብዮታዊ ዲሞክራሲያውያን ጋር አብረው እነሆ ሊያጠፏት ዘምተውባታል፡፡
ታላቋ ሀገራችን ኢትዮጵያም እንዲሁ ተዘምቶባታል፡፡ ለፍቅር ሳይሆን ለጥላቻ፣ ለእርቅ ሳይሆን ለበቀል፣ ወደ አንድነት ሳይሆን ወደ መበታተን የሚወስዳት የእነ ዮዲትና ግራኝ ውላጆች፣ የእነ ሞሶሎኒ ደባና ሴራ ራሱን አዘምኖና አደራጅቶ በማን አለብኝነት ዳግም ህልውናዋ ላይ ተዘምቶባታል፡፡
እነሆ ዛሬ፤
፨ ለእኛ እንደ አቤሜሌክ የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን እና የታላቋን ኢትዮጵያ ሀገራችን ከተደቀነባቸው የወል ጥፋት የሚሰውረን እንደ ኤርምያስ ያለ ነቢይ ከወዴት እናገኝ ይሆን? እንደ ጻድቁ አባታችን እንደ አቡነ ጴጥሮስ ተዋሕዶን ለተኩላ፣ ኢትዮጵያን ለባንዳ አሳልፈን እንዳንሰጥ የሚገዝተን ጀግና መሪ ወዴት እናመጣ ይሆን?
፨ ዛሬ እንደ ቀደሙት አባቶቻችን ትናንት የክርስትና መሰረት እና ደሴት ለነበሩት ዛሬ ግን በግፍ የሚረግፉትን የሶርያና የግብጽ ክርስቲያን ወንድሞቻችንን መታደግ ባንችልም፤
፨ በሀገራችን ገዳማቱና አብያተ ክርስቲያናቱ በቃጠሎ ሲወድሙ፣ ካህናቱና ምዕመኑ በቀያቸው እንደ በግ ሲታረዱና በግፍ ሲሳደዱ፣ ግድ የሚለው የቤተ ክርስቲያን መሪ እንዲሁም የዜጎቹ መሳደድ የሚያሳስበውና ሀገራዊ ኃላፊነት የሚሰማው መንግሥት እና ተቋም የኖራል በሚልና ለችግሮች ሁሉ ተገቢው መፍትሔ በሚመለከተው አካል ይሰጣል በሚል በኢትዮጵያዊ ጨዋነትና በክርስቲያናዊ ሆደ ሰፊነት ፍትህን በትዕግስት መጠበቃችን፤
፨ ቅዱስ ሲኖዶሱ በመንግሥት ባለሥልጣናት ሲደፈርና ብፁዓን አባቶቻችን በዘመኑ ጋጠወጦች ሲጎሸሙና ሲዋከቡ፣ ይልቁንም ለዘመናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በሁለት ሲኖዶስ ስር እንድትቆይ ያደረጋትን ውጫዊ ሴራ ለማክሸፍ አባቶቻችን በተጉ ጊዜ በመንግሥት አላስፈላጊ ጣልቃ ገብነትና በቤተ ክህነቱ ውስጥ በተሰገሰጉ የፕሮስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆች ደባ የዕርቁ ሂደት ሲከሽፍ እያየን እንዳላየን ማለፋችን፤  
፨ ይልቁንም በአለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ቤተ ክርስቲያናችን ከየአቅጣጫው ከተጋረጡባት የመናፍቃን የተቀነባበረ ወረራና ጥቃት፣ ከአክራሪ እስልምና ጅሃዳዊ ዘመቻ፣ በእቅፏ ተሰግስገው ከሚገዘግዟትና  በጎጥ ተደራጅተው ከሚቦጠቡጧት ሙሰኛ ካድሬዎች ዘረፋ ከመታደግ መዘግየታችን፤ ወዘተ ያሳበየው የጥፋት ሃይል፤
በሌላ በኩል፤
፨ ጥንታዊ ገዳማቶቻችን በቀለብ፣ በአልባሳት፣ በውኃ፣ በመብራት፣ በንዋየ ቅድሳት፣ ወዘተ እጥረት እንዳይዘጉና ቅዱሳን አባቶችና እናቶቻችን እንዳይሰደዱ፤ የአብነት ጉባዔያት በመምህራን ደሞዝ፣ በተማሪዎች ቀለብና አልባሳት ማጣት ተማሪዎች እንዳይበተኑና ቤተ ክርስቲያናችን ተተኪ እንዳታጣ፤
፨ ይልቁንም በሀገራችን ከተማሪው አብዮት ጋር ተያይዞ በተከሰተውና ዘመን በወለደው የግራ ዘመም የፖለቲካ አስተሳሰብ ምክንያት ከክርስቲያናዊ ሕይወት በተጻራሪው የሚሄደውንና እንደዋዛ የተፈጠረውን የትውልድ ክፍተት ለመሙላት፣ እንዲሁም ወጣቱን ትውልድ ከተጀመረው የክህደት ቁልቁለት ለመታደግ በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማቱ ሌት ከቀን እየባዘነ ያደራጀ፣ ያስተማረና፣ ቤተ ክርስቲያን የወላድ መሐን እንዳትሆን የታደገን ክፍል፤
፨ አንዳንድ አምባገነን የመንግሥት ባለሥልጣናት በተለያዩ መድረኮች ያለ ስሙ ስም፣ ያለ ምግባሩ ምግባር በመስጠት ለመወንጀል ሲሞክሩ በዝምታ መመልከታችን ቤተ ክርስቲያናችንን በሚመሩት አባቶቻችን ጭምር ሲነገር መስማታችን አስደንጋጭ ከመሆኑም ባሻገር መጭውን ጊዜ ከወዲሁ በአንድነትና በጥንቃቄ እንድንመረምርና የመፍትሄ አቅጣጫም እንድናስቀምጥ የግድ የሚል ሆኖ ይሰማኛል፡፡
ስለሆነም ሁላችን የተዋሕዶ ልጆች በአንድነት በማኅበረ ቅዱሳን አባላትና አመራሮች ላይ የተከፈተውን የስም ማጥፋት ዘመቻ በማውገዝና በመንግሥትና በቤተ ክህነቱ ውስጥ ተሰግስገው በሚገኙ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆች አማካኝነት እየተወሰደባቸው ያለውን የማዋከብና የማሸማቀቅ እርምጃ በአስቸኳይ እንዲቆም አስፈላጊውን የተቀናጀ እንቅስቃሴ ከወዲሁ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ካልሆነ የአቤሜሌክ የልጅ ልጆች የሀገራችንና የቤተ ክርስቲያናችንን ጥፋት በዓይናችን ከማየት ማን ይታደገን ይሆን?
በመጨረሻም፤
ምን አልባት ለዘመናት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ ሰፍኖ የኖረው እና እንደ ታሪካዊ እርግማንና ውርደት የምቆጥረው በአባቶቻችን ላይ የተፈፀመው የመከፋፈልና የማሰደድ ስትራቴጂ በማኅበረ ቅዱሳን አመራሮች ላይም ለመድገም መታሰቡና የማኅበሩንም ቢሮ ለመዝጋት ብሎም በተለጣፊ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆች ለመተካት የተጠነሰሰው ሴራና በቅርቡም በኢቴቪ እየተሰራነው የሚባለው “ማኅበረ-ቅዱሳናዊ ሐረካት” ፊልም ለሚያመጣው ውዝፍ መዘዝ ብቸኛው ተጠያቂ አሁን በሥልጣን ላይ የሚገኘው የሀገሪቱ መንግሥትና የመንግሥቱን አመራር በበላይነት የያዘው ኢሕአዴግ ብቻ መሆኑን ከወዲሁ ማስገንዘብም ማሳሰብም ወደድኩ፡፡
  
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
መጋቢት ፳፩, ፻፪፲፬
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

  (By “Abel Sog Sos”)

እስኪ እውነቱን እንነጋገር!
አሁን ባለንበት ዘመን ሃገርን ስለመውደድ የምንማረው/የተማርነው ከየት ነው? ከቤተ እምነቶች ወይስ ከስነ ዜጋና ስነ ምግባር ወይም “ሲቪክስ” ኮርስ? የጸረ ሙስና ኮሚሽን ሳይቋቋም ማን ነበር የራስ ያልሆነን ስላለመውሰድ ያስተማረው? አሁንስ ቢሆን? የሃይማኖት ተቋማት አይደሉምን?

እድሜ ለማኅበረ ቅዱሳንና ወጣቱ በየግቢጉባዔያቱ ተኮትኩቶ ባይወጣ ምን ይውጠን ነበር? አገሩ ሁሉ ሙሰኛ በሙሰኛ ይሆን አልነበር! (መንግስት እንዲያውም ቢያውቅበት ሊደግፈው ይገባ ነበር፤ የ’ርሱን ስራ ማኅበረ ቅዱሳን እየሰራለት ስለሆነ!)
በመልካም ገጽታ ግንባታ (የተዋስኳት ከኢቲቪ ነው።) ከመንግስት ባልተናነሰ የሃገር ሃብት የሆኑ ቅዱሳት መካናትን ጠብቆ በማቆዬት የአንበሳውን ድርሻ ማኅበረ ቅዱሳን አይወስድም?
የእናት ጡት ነካሽ ፖለቲከኛ ሁላ ዛሬ ማኅበሩን አፍርሰው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንን የተኩላ መፈንጫ ለማድረግ ከላይ ታች ማለቱን ተያይዘውታል፤ ቤተክህነቱ ውስጥ በተሰገሰጉ “አማኝ መሳይ” ካድሬዎች በኩል።
በጣም የሚገርመኝ ነገር ቢኖር በቁም ሳሉ ሊያፈርሷት የታተሩ ሁሉ በኋላ ግብአተ መሬታቸው እንደ ሥላሴ ባሉ ታላላቅ ካቴድራልና አድባራት ሲፈጸም “እገሌ ታላቅ ሰው ነበሩ። እትት እትት” ተብሎላቸው ይቀበራሉ። የሚቀብሯትን የምትቀብር ቤተክርስቲያን!
ማኅበረ ቅዱሳንን መቅበር ማሰብ ከብርቱውና ኃያሉ አምላክ ጋር መታገል ነው፤ እግዚአብሔር ወድዶና ፈቅዶ የመሰረተው ማኅበር ነውና።


Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

 
·ዕለቱ አርብ ነው!
ኢየሱስ ይሰቀል!
ይሰቀል ኢየሱስ!
በርባን ግን ይፈታ!
2 ሺህ ዘመን
ይኸው ትጮሃለች
ዓለም አፍ አውጥታ።

በቀያፋ ምክር 
በካህናት አድማ
በጲላጦስ ስልጣን 
በግፈኞች ጡጫ
ዛሬም ይወገራል 
ጌታ ይሰቀላል።
እውነት ነው!
በድምጽ ብልጫና
በቲፎዞ መድረክ
ለምትመራ ዓለም
ሌባውን አንግሶ
ንፁሁን ከመሸጥ
ሌላ አይጠበቅም።
መጋቢት 2006 .ዓም

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


ለነሱ (ለማ/ቅዱሳን) የተሰጠው ስም ለእኔም ይገባኛል

(ክቡር አቶ ግርማ ሰይፉ፤ የፓርላማ አባል)
ክቡር ሆይ
አኔ የአንድ እምነት አንድ ሀገር አራማጅ ነኝ መንግ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ ዘመቻ ጀመረ በሚል እሰጥ አገባ እንደበዛ አውቃለሁ፡፡ በሌለኝ መረጃ የእኔን ስም እየጠቀሱ ሰዎች ፖስት እንደሚያደርጉ ከሰዎች ብሰማም የእኔ ፌስ ቡክ ይህን አልገለፀልኝም፡፡ ለማኛውም መንግሥት በእምነት ላይ ዘመቻ ሲጀምር በኦርቶዶክስ ላይ በማኅበረ ቅዱሳን መስመር እንደነበር ትዝ ይለኛል፡፡ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒሰትር አቶ መለስ ይህን አሰመልክተው ለሰጡት አሰተያየት የሰጠሁትን ምላሽ በድጋሚ ላጋራችሁ፡፡ ይህ ነው የእኔ አቋም፡፡ ይህ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ከገጠመ እሰየው ነው፡፡ ለነሱ የተሰጠው ስም ለእኔም ይገባኛል፡፡ የሰጠሁት ምላሽ እንደወረደ ይህን ይመስል ነበር፡፡


ብዙ ጉዳዮች እንደተርጓሚው እንደሚሆን መገመት ይቻላል ነገር ግን አንድ እምነት አንድ ሀገር ማለት ግን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እንተረጎሙት ሳይሆን፤ አንድ ሰው ሊኖረው የሚገባው አንድ ምነት ብቻ ነው (ሰኞ፤ ዕሮብና አርብ ሙስሊም ማክሰኞ፤ ሀሙስና ቅዳ ክርስቲያን፤ ወዘተ መሆን አይቻልም) ይህ ደግሞ አምላካዊ ቃል ነው(እኔ ቀናተኛ አምላክ ነኝ ሲል) ይህ አምላካዊ ቃል ደግም የሚሰራው ለሚያምኑበት ነው፡፡ ቃልቻ ቤት እየሄዳችሁ ቤተ ክርስቲያን አትምጡ ማለት ነው፡፡ ሊኖረን የሚገባው አንድ እምነት ነው፡፡ በእርግጠኝነት ሙስሊም ሆኖም ክርስቲያን መሆን አይቻልም ለዚህ ይህ ለአንድ እምነት የመገዛት ፍልስፍና የሁ የእምነት ዘርፎች መለያ ነው፡፡ ጥንቆላ ብቻ ነው ይህንን የሚፈቅደው ይህ ደግም በሁሉም እምነቶች የተወገዘ የመጥፎ መንፈስ ነው፡፡ ለዚህ እኔ ያለኝ አንድ እምነት ብቻ ነው፡፡ መፍክሬም ነው፡፡

ከአንድ እምነት ጋር ተያይዛ የመጣችው የአንድ ሀገር ጉዳይ ነው፡፡ ይህ በእርግጥ አከራካሪ ነው፡፡ አንድ አንድ ሀገሮች ጥምር ዜግነትን የሚፈቅዱ አሉ ይህም ሆኖ እኔ በግሌ ኢትዮጵያ ከምትባል ሀገር በሰተቀር ሌላ ሀገር የለኝምእንዲኖረኝም አልፈልግም ይህን አቋሜን ገልፅ ግን እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ ስል ሌሎች ኢትዮጵያዊ አይደላችሁም አለ ተብሎ ልከሰስ አይገባም፡፡ አንድ የእስልምና እምነት ተከታይ ኢትዮጵያዊ ሊሆን እንደሚችል ብዥታ ኖሮብኝ አያውቅም ወይም የሌላ ክርስትና እምነት ተከታዮች ኢትዮጵያዊ ንደሆኑ አልጠራጠርም፡፡ አማኒያንም ቢሆኑ፡፡
አንድ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አለችኝ ብዬ ነው ለዚህች ሀገር እድገት (ሁሉ አቀፍ እድገት ማለቴ ነው) የሚከፈል መሰዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ የሆኑኩት፡፡ ሌላ አማራጭ የለኝምአማራጭ ያለው ግን ካልተመቸው ወደዛኛ ሊሄድ ይችላል፡፡ ሁለት ጉርጓድ ያላት አይጥ እንደሚባለው፡፡ እኔ ግን ሀገሬ አንድ እና አንድ ነች፡፡ ኢትዮጵያ፡፡ ይህ ማለት ግን በምንም መመዘኛ ይህች ሀገር የኔ ብቻ ነች ማለት አይቻልም፡፡ አይሆንምም፡፡ እኔ የአንድ እምነት እና አንድ ሀገር ባለቤት ነኝ፡፡

ምንጭ፦ የፌስቡክ ገጻቸው።

 

Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 22/2006 ዓ.ም፤ ማርች 31/2014. PDF)፦ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ሰጠው። ምህሩንና ጌታውን ክዶ፣ ስሞ ለግርፋት እና ለመስቀል ሞት ተስማማ። ይህንን የጌታን ሕማማት፣ ስቅላት፣ ሞትና ትንሣኤ በምናስብበት በአሁኑ ወቅት ማኅበረ ቅዱሳንን ለሕማም፣ ለስቅላት እና ለሞት አሳልፎ ለመስጠት የሚደረገው ትርምስ ተጀምሯል። ይሁዳ ለ30 ዶላር እነዚህ የዘመናችን ሰቃልያን ደግሞ “ማኅበሩ ያፈራውን ሀብት በሙሉ ለመዝረፍ ጊዜው አሁን ነው” ብለዋል። በዚህም በዚያም ክህደት እና ስቅለት።

መጋቢት 13/2006 ዓ.ም “በዓይነቱ ለየት ያለ” ስብሰባ በቤተ ክህነቱ ግቢ ተካሒዷል። ለየት ያለ የተባለው አጀንዳውና ቁመነገሩ ሳይሆን ቤተ ክህነቱ ባልለመደው ሁኔታ፣ ከቤተ ክህንቱ ይትባህል ውጪ በዐቢይ ጾም ወቅት ዩየተደረገ የ“ስቅሎ ስቅሎ ስብሰባ” (የስቀለው ስቀለው ስብሰባ) መሆኑ ነው። ፋክት መጽሔት “ለመጽሔቱ ዝግጅት ክፍል የደረሰው በድምፅ የተቀረፀ የውይይቱ ሙሉ ክፍልን ጠቅሶ እንደገለጠው ተሰብሳቢዎቹ ማኅበሩን በተመለከተ ያወጡት የአቋም መግለጫ÷

  • የማኅበሩና የዋነኛ መሥራቾችና አባላት የባንክ አካውንት፣ ቀላልና ከባድ ተሸከርካሪዎች ጨምሮ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረቶች፣ /ቤቶች፣ የንግድ ተቋማት፣ የአክስዮን ተቋማት፣ የንዋያተ ቅድሳት ማምረቻዎችና ማከፋፈያዎች፣ ከቀረጥ ነጻ የገቡና በመግባት ላይ ያሉ ዕቃዎች በሚመለከታቸው የመንግሥት መሥ/ቤቶች እንዲታገዱ በቅ/ሲኖዶስ አማካይነት ደብዳቤ እንዲጻፍ፤
  •  ከምእመናን በቀጥታም ኾነ በተዘዋዋሪ የሚቀበለው ዓሥራት እየፈረጠመበት ስለኾነ እንዳይቀበል ይከልከል፤
  • የግቢ ጉባኤያት (የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት) እርሱ በሚቀርፀው ትምህርት እንዳይወሰዱብን በደንብ መሥራት፤
  • ተጠሪነቱ ከዋና ሥራ አስኪያጅነቱ ሥር ወጥቶ በሰንበት /ቤቶች /መምሪያ ውስጥ አንድ ንኡስ ክፍል ይኹን የሚሉና የመሳሰሉት ይገኙበታል፡፡

የተሰብሳቢዎቹ ማንነት እና ምግባራቸውን ለጊዜው ብንተተውና ጥያቄያቸውን ብቻ ተመርኩዘን ብንወያይ እንኳን ብዙ ሐጸጽ እና ኢ-ኦርቶዶክሳዊ ተግባራትን ማግኘት እንችላለን።
በዚህ በዐቢይ ጾም የሱባዔ ወቅት እንዲህ ያለውን የአድማ ስብሰባ ለማካሔድ ሲጠይቁ ፈቃድ የሰጠው አካል አንድም ቤተ ክህነቱንና ቤተ ክርስቲያኑቱን አያውቅም ወይም አያምንባትም፤ አንድም ከአቅሙ በላይ የሆነ ተጽዕኖ ተደርጎበታል። ሌላው ሁሉ ቢቀር አዲሱ ፓትርያርክ በዚህ የአመጽ ተግባር ላይ እጃቸውን አስገብተው መገኘታቸው ለዘመነ ፕትርክናቸው ትልቅ ጥቁር ጠባሳ ያስቀምጥባቸዋል። ምን ይሉኝ ማለት የማያውቁት ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንኳን (አፈር ይቅለላቸውና) እንዲህ ያለ ስሕተት ሲሳሳቱ ታይተው አይታወቁም።
የማኅበሩ ንብረት ለመሆኑ የማን ነው?
ይህንን በሥርዓት አስረግጦ መመለስ ያስፈልጋል። ደጀ ሰላም እስከምትረዳው ድረስ ማኅበሩ ሕጋዊ ሰውነት ያገኘው ከቤተ ክርስቲያኒቱ ነው። ቤተ ክርስቲያን ይሁነኝ ብላ ያቆመችው፣ ነፍስ የዘራችበት ማኅበር ነው። በአገሪቱ ሕግ መሠረት ማንኛውም ተቋም ሕጋዊነት ሳይኖረው መንቀሳቀስ አይችልም። ማኅረሩ ቅዱሳን በኤን.ጂ.ኦ ሕግ በመንግሥት መዝገብ ፈቃድ ያወጣ ሳይሆን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው ፈቃድ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና የሚንቀሳቀስ ነው።
በምሳሌ እናስረዳ። አራዳ ጊዮርጊስ ያስገነባው ሕንጻ፣ የልደታ ቤተ ክርስቲያን ግንቦች፣ የምስካየ ኅዙናን  ገዳም ት/ቤት የማን ንብረት ናቸው ተብሎ ይጠየቃል? አቡነ ጳውሎስ ያሠሩት መንበረ ፕትርክናው የማን ነው ተብሎ ይጠየቃል? አንዱ ገዳም እርሻ ቢኖረው የማን እርሻ ነው ይባላል? እንዲህ የሚል ሰው ቢመጣም መልሱ ቀላል ነው። “ይህ ንብረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ነው” የሚል ነው።
የምስካየ ኅዙናን ገዳም ት/ቤት የቤተ ክርስቲያኒቱ ቢሆንም የማስተዳደር ኃላፊነቱ የገዳሙ ነው። የአራዳ ጊዮርጊስ ንብረት፣ የመርካቶው ራጉኤል ሕንጻዎችም ወዘተ ወዘተ የቤተ ክርስቲያን ናቸው የሚያስተዳድሯቸው ግን አጥቢያዎቹ ናቸው።
ታዲያ የማኅበረ ቅዱሳን ንብረት የተለየ እንደሆነ ተደርጎ የሚቀርበው ለምንድነ ነው? የቤተ ክርስቲያን ንብረት መሆኑ እየታወቀ፣ ነገረ አስተዳደሩ በማኅበሩ ጠቅላላ አባላት ምርጫ በሚሰየሙ የሥራ አመራር እና የሥራ አስፈጻሚ አካላት መሆኑ እሙን ሆኖ ሳለ የሌላ አካል ሀብት እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ለምን አስፈለገ?
መልሱ ግልጽ ነው። ንብረቱን ለመዝረፍ፣ ሀብቱን ለመመዝበር ያቆበቆበ፣ የቋመጠ፣ የአጥቢያዎችን ንብረት በመዝረፍ ሚሊዬነር የሆነ የብላው እንብላው ቡድን ፍላጎት ነው።
አዎ፣ ማኅበሩ ከአባላቱ ላብ ባገኘው የፈቃድ ድጋፍ እና አገልግሎቱ በገባቸው ኦርቶዶክሳውያን ርዳታ ሕንጻውን ጨርሷል። አሁን ሲያዩት ያጓጓል። ለእነ ሆድ አምላኩ ዝርፊያ የማይመች ይህንን የመሰለ ነገር አይቶ ማለፍ አይቻላቸውም። ስለዚህም አይሁድ ጌታን በሰላላ ዲናር ክህደት ለመስቀል ሞት እንዳበቁት፤ በግዑ ለእግዚአብሔር (የእግዚአብሔር በግ) ክርስቶስን አርደው ሳይበሉት እንደቀሩት፣ እነዚህ የዘመናችን ተረፈ አይሁድም ማኅበረ ቅዱሳንን ለመስቀል ቋምጠዋል። ላይበሉት፣ ላይጠቀሙበት።
ማኅበሩ አጠቃላይ የገቢና የወጪ ሥርዓቱን የሚያካሒደው ዘመኑ በፈቀደው ጥበብ ሁሉ እንጂ ጊዜ ባለፈበት እና ለዝርፊያ እና ለሙስና በተጋለጠ ያረጀ ያፈጀ የሒሳብ አሠራር አይደለም። እነዚህ ሰቃልያንና ዘራፍያን ይህንን ያውቃሉ። ገንዘቡ እኛ በምንፈልገው መልክ ይሰብሰብ ማለታቸው ለዚያ ነው።
አሁን ስለተጀመረው የቤተ ክህነቱ የመዋቅርና አስተዳደራዊ ለውጥ እና በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለተስፋፋው ዝርፊያ በቅድስት ማርያም ዩኒቨርስቲ የአካውንቲንግ መምህር እና በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሦስተኛ ዓመት ተማሪ” የሆኑት አቶ ምሐባው ዓለሙ ለአዲስ ጉዳይ መጽሔት ያሉትን ለማስረጃ እንጥቀስ።
“ስለ ፋይናንስ ሥርዓቱ ሲነሣ ብዙ ሰዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ የምትጠቀምበት ዘመናዊ አሠራር (double entry) ይመስላቸዋል፡፡ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን አኹን እየተጠቀመችበት ያለው የፋይናንስ ሥርዓት ዓለም በ፲፯ኛው // የተወውንና የነጠላ ሒሳብ አሠራር (single entry) የሚባለውንና በሞዴል የሚሠራ የሒሳብ አሠራር ነው፡፡ በዓለም ላይ እንዲኽ ዓይነት የሒሳብ አሠራር የሚከተል ምንም ተቋም የለም፡፡ በመኾኑም ይኼን ተረድቶ የፋይናንስ ሥርዓቱን ማዘመን ይገባል፡፡ ይኼ የሒሳብ አሠራር በፍጹም ምቹ አይደለም፡፡ የሒሳብ አሠራሩ በራሱ ነጠላ ነው፡፡ ወጪን ወጪ ይላል እንጂ ምክንያቱን አይናገርም፡፡ ስለዚኽ ወጪን ከነምክንያቱ ገቢን ከነምንጩ የሚጠቅሰው የሁለትዮሽ (ደብል) አሠራር ሥርዓት የላትም፡፡ ይኼ አሠራር ደግሞ በአፋጣኝ መለወጥ አለበት፡፡”
ግለሰቡ “የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች”የሚልና ስለ ዝርፊያው ጥልቅ ምንነት አይን ገላጭ የሆነ ማስረጃ ያቀረቡ ናቸው። ዝርፊያው ምን ያህል የጎላ መሆኑን ሲያብራሩ ያሉትን እናክል፦
አዲስ ጉዳይ፡- በአኃዛዊ ስሌት የገንዘብ ዘረፋው ምን ያህል ይደርሳል?
 አቶ ምሐባው፦ እኔ በየዓመቱ ቤተ ክርስቲያን በመቶ ሚልዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ትመዘበራለች ብዬ በመጽሐፌ ላይ ገልጩ ነበር፡፡ ይኹን እንጂ አሁን ከቀድሞ በተሻለ ጉዳዩን ስመለከተው ቤተ ክርስቲያን በምዝበራ የምታጣው ሀብት ከመቶ ሚልዮኖች የሚልቅ መሆኑን ለመረዳት ችያለሁ፡፡ (አዲስ ጉዳይ፤ ቅጽ 8 ቁጥር 206፤ መጋቢት 2006 ዓ.ም.)
በዚህ ምዝበራ ላይ የተሰማሩት እነማን ናቸው? ፖለቲካዊ አቋማቸው ምንድነው? ይህ ሁሉ ሚሊዮን እና ሚሊዮን የምእመናን ላብና ደም፣ የቤተ ክርስቲያን ንብረት የሚዘረፈው በነማን ነው? ብለን ትንሽ ገፋ አድርገን ስንጠይቅ ከፍ ብለን የጠቀስነውን የአመጽ ስብሰባ ወደሚያደራጁት አካላት እንመጣለን።
ታዲያ ይሄ የዘረፋ ቡድን፣ በመንግሥት ጥበቃ እንዴት ሊያገኝ ቻለ? የፓርቲያቸው አባላት የሆኑ ሰዎች በቤተ ክርስቲያን ዝርፊያ ላይ ሲሰማሩ አበጃችሁ እየተባሉ ከአባላት ድጎማ በመሰብሰብ በሚያገኘው ሳንቲም ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚረዳ ስብስብን ለማጥቃት ዘመቻ ሲጀመር መንግሥታዊ ጥበቃ አለማድረግ በዘመቻው ከመተባበር ተለይቶ አይታይም።
ከሁሉ ከሁሉ አዲሱ ፓትርያርክ እና አዲሱ አስተዳደራቸው እየተከተለ ያለው አካሔድ ግን ያልተጠበቀ ባይሆንም ለታሪካቸው የማይበጅ እና አሳፋሪ የሚባል ነው። በየሳምንቱ አዳዲስ ደብዳቤ ለማኅበረ ቅዱሳን ለማብረር የማይደክሙ ሰዎች ምእመናንን የሚጠቅም ሥራ ለመሥራት እጃቸውና እግራቸው ሲተሳሰር ማየት ያሳፍራል። “በነገሩ የለሁበትም” እያሉ የሚምሉ የሚገዘቱት አቡነ ማቴዎስም (ሥራ አስኪያጅ) ሆኑ ፓትርያርኩ አቡነ ማቲያስ ከታሪክ ተወቃሽነት ሊያመልጡ አይችሉም።
ቢያንስ ቢያንስ “ኧረ ዐቢይ ጾም ነው፤ ሰው ምን ይለናል” ማለት ማንን ገደለ? ወይስ የቆሎ ተማሪው “ቀራንዮም ቀራንዮ፤ ካህናቱም ካህናቱ” እንዳለው ሆነ? ታሪክ፦ተማሪው ፍርፋሪ ፍለጋ  በእንተ ስማ ለማርያም እያለ ወደ ቀራንዮ ቤት ክርስቲያን ሄደ አሉ።፡ከዚያ ካህናቱ ሳይራሩለት ይቀራሉ። እያዋዛ መናገር የሚችለው ተማሪም “ቀራንዮም ቀራንዮ፤ ካህናቱም ካህናቱ” አለ ይባላል። አሁንም በዚህ የጌታ ጾም እንደቀደሙት ካህናተ አይሁድ “ስቅሎ ስቅሎ” ማለት በስምም በግብርም አያመሳስላችሁም? ቤተ ክርስቲያንን ብሎ የተሰበሰበው ይህ ትውልድ ግን በዳዊት ቃል፦
“”ፍታሕ ሊተ እግዚኦ አምላኪየ በከመ ጽድቅከ፤
ወኢይትፈስሑ ላዕሌየ።
አቤቱ አምላኬ እንደ ጽድቅህ ፍረድልኝ፤
በላዬም ደስ አይበላቸው” (መዝ 35፡24) እንደሚል ባይዘነጉት ግሩም ነው።
ቀጥሎም፦
“ሐሰስክዎ ለእግዚአብሔር ወተሰጥወኒ፤
ወእምኵሉ ምንዳቤየ አድኀነኒ፤
እግዚአብሔርን ፈለግኹት መለሰልኝም፤
ከመከራዬም ሁሉ አዳነኝ።” (መዝ. 33፡ 4) ማለቱ አይቀርም። እግዚአብሔርን ያለ ትውልድ ነዋ።
ጆሮ ያለው ይስማ።
ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 20/2006 ዓ.ም፤ ማርች 29/2014/ PDF)፦ ሥርዓተ ቅዳሴውን ለመምራት  ተሰይመው ለተመለከታቸው ከረጅሙ ነጭ ጽህማቸው  ጋር ውብ  የሆነውን  መረዋ  ድምጽ ሲሰማ ምድራዊ  ሳይሆን  ከሰማይ የተገለጠ መልአክ ይመስሉ ነበር፡፡ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት የተለየ ፍቅር ስለነበራቸው በተጋበዙበት መድረክ ሁሉ አክብረው በሰዓቱ ይገኛሉ፡፡ ለማስተማር ከተነሱም በትርጋሜ  የተዋዛ  ምስር አዘል ትምህርታቸውን ለምእመናን ቀምመው ያቀርባሉ፡፡ ለሃይማኖት ያላቸውን ቀናዊነት ለመረዳት በትምህርታቸው መግቢያ  የሚናገሩትን  መልእክት መስማት ብቻ በቂ ነው፡፡ ይህ የመግቢያ መልእክታቸው ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ልተበረዘች ያልተከለሰች  መሆን የሚስረዱበት በተለያዩ ዘመናት የተነሱባትን መናፍቃን በመጥቀስ እነዚህ ሁሉ ያልበረዛት ያልከለሳት መሆናን የሚገልጹበት ነው፡፡ እናም በጥዑም አንደበታቸው ስለቤተ ክርስቲያን ሲናገሩ ለሰማቸው  የሊቃውንቱ ዘመን የእነ እትናቴዎስ ዘመን የሃይማኖት ቅናት በውስጣቸው እንዳለ ይረዳል፡፡ ብፁዕ አቡነ ቶማስ፡፡

በደብረ ሊባኖስ ገዳም መጻሕፍተ ሊቃውንትን ረዘም ላለ ጊዜ  በማስተማር  ቆይተው ነው  ወደ አዲስ አበባ የተዛወሩት፡፡ በገዳሙ ውስጥ ሲኖሩ የነበራቸውን መንፈሳዊ ሕይወት እና አንድምታውን የማስተማር ብቃት በወቅቱ የነበሩ አባቶች የሚመሰክሩት በታላቅ አድናቆት ነው፡፡ ሊቅነትን  ከመንፈሳዊነት   ጋር ይዘው በመገኘታቸውም ቤተ ክርስቲያን ለበለጠው አላፊነት አጭታ ለጵጵስና ማዕረግ በቅተዋል፡፡ መናፍቃንን  በተመለከተ ግልጽ የሆነ ቀጥ  ያለ አቃም ነበራቸው፡፡ፀረ  ማርያም  የሆነን  የተሐድሶ ጭፍራ መታገሥ አይችሉም፡፡ በቅዱስ ውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የነበረውን የተሐድሶ እንቅስቃሴ ሥሩን ነቅለው የጣሉበት የዲንነት ዘመናቸው ለዚህ ምስክር ነው፡፡ እንደእነ ቅዱስ ቄርሎስ የመናፍቃን መቀጥቀጫ መዶሻ ነበሩ፡፡ ላ ይህ ቀናነታቸው እና  አድርባይ ሊሆኑ ያለመቻላቸው ጉዳይ  በቤተ ክህነቱ ውስጥ በተሰገሰጉ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ስላልተወደደላቸው እንዲጠሉና እንዲገለሉ አድርቸዋል፡፡ ፓትርያክ አቡነ ጳውሎስ  ምርጥ ምርጡን ለወዳጆቼ በሚሉበት እንዳሻቸው ሃገረ ስብከት በሚያድሉበትም ዘመን አቃማቸውን ብዙም ስሎማይወዱላቸው ጠረፋማ ሥፍራዎች  ላይ እንዲመደቡ ሆነዋል፡፡ለነገሩ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ስለሚመደቡበት ሃገረ ስብከት ብዙም የሚጨነቁ  ስላልሆኑ ወደተላኩበት ሁሉ በደስታ  ይሄዳሉ፡፡ ፍሬም ያፈራሉ፡ቤተ ክርስቲያን የሰው ያለህ በምትልበት በዚህ ወቅት እንዲህ ያለ አባት ማጣት ትልቅ ሀዘን ነው፡፡ ብፁዕነታቸው ወደ አገለገሉት አምልክ በክብር ቢሄዱም እኛ ግን በትልቁ ተጎድተናል፡፡
ወቅቱ በአጠገባችን ያሉ ጥቂት መንፈሳዊ አባቶችን በስስት የምንመለከትብት ነው፡፡አይቴ ሀለ ቀደምት ጳጳሳት የቀደሙ አባቶች ደጋጎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ወዴት አሉ?” እያልን ዘመን ገድባቸው የተለዩንን በሀዘንና በቁጭት የምናስታውስበት ነው፡፡ በግል ቂምና በቀል ተ ክርስቲያንን ለመናፍቃን አሳልፈው የማይሰጡ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚገባቸውን መከራ ሁሉ በጥብዓት የሚቀበሉ፣ ከአላውያን ነገሥታት እምነት የለሽ መንግሥታት ጋር የማይዛመዱ፣ በፍልስፍናና በምድራዊ ተድላ ተይዘው  በእምነት ጉዳይ  ቸልተኛ ያሆኑ፣ መስሎ ለማደር ሲሉ ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጋር የማይተባበሩበሚያልፍ ጊዜ የማያልፍ የታሪክ ጠባሳ ለትውልዱ ላለመተው የሚጠነቀቁእኔ ካልተነካ ሕዝቡም ሆነ አገልጋዩ ያሻውን መከራ ቢቀበል ምን አግብቶኝ ሲሉ የማይገኙ አባቶችን ተጠምተናል፡፡
እንደ ሙሴ ሕዝብህ ከሚጠፋ እኔን ከይወት መጽሐፍ ደምስስ የሚሉ፣ እንደ ነ  ኤልያስ  ስለ እግዚብሔር ክብር የሚቀኑ፣ እንደ ነዩ ዳዊት የተቀመጡበት ዙፋን የሚኖሩት የተድላ ኑሮ የተነሱበትን የማያዘናጋቸውበመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ላፊያትና መጻዕያትን የሚረዱ፣ ሳይነገራቸው የመናፍቃንና የአላውያን ነገሥታት የጥፋት አካሄድ የሚገባቸው፡፡ እንደ ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔር በክብሩ ዙፋን ተቀምጦ የሚታያቸው፣ ከምድራዊ ነገሥታት ከመዘመድ ይልቅ አደራውን ለሰጣቸው ለሰማዩ  ንጉሥ  መታዘዝ እንደሚበልጥ የሚረዱ፡፡ እንደ ሐዋርያት እስከ ሞት የሚታመኑ፡፡ እንደ ሊቃውንት መናፍቃንን የሚገስጹ አልመለስ ያሉትንም የሚያወግዙ አባቶችን ተጠምተናል፡፡
የቤተ ክርስቲያን አምክ ነገን እንደ አትናቴዎስ ያለ አትናቴዎስ፣ አባ ጊርጊስ ዘጋስጫን የሚተካ ሌላ አባ ጊርጊስ  እንዲተካ አጥብቀን  እንለምነው፡፡ ለእርሱ ምን ይሳነዋል? ይህ ሁሉ ወጀብ አልፎ ደግ ዘመን ያመጣልን ይሆናል፡፡ ለሁሉም በሕይወት ያሉትን  ለተዋሕዶ ጠበቃና አርበኛ የሆኑ አባቶች ድሜ ያርዝምልን፡፡ ያረፉትን አባቶች በረከትም በያለንበት ያድለን፡፡ አሜን፡፡                                                                                                                        ቸር ወሬ ያሰማን፤ አሜን።  ቸር ወሬ ያሰማን።
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 19/2006 ዓ.ም፤ ማርች 28/2014/ PDF)፦ በዚህ የዘመነ ብላ ተባላ፣ ጸረ ሊቃውንት እና መፍቀሬ ተሐድሶ ዘመን በቤተ ክህነት ከቁንጮው እስከ ግርጌው ባሉ በልቶ አደሮች ሲገፉ ከኖሩት አባቶች መካከል አንዱ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ነበሩ። አፈር ይቅለላቸው። ዕረፍታቸው እጅግ ቢያሳዝነንም ማንም ከዚያ ስለማይቀር የምንጸጸትበት አይደለም። እንዲህ የተማሩ ሊቃውንት እንደ ተርታ ሰው ወደጎን ተገፍተው ዳዊት ባልደገመ አፋቸው ነገረ ቤተ ክርስቲያንን የሚዘነጥሉ፣ ንብረቷን የሚዘርፉ፣ አሰረ ክህነታቸውን ያልጠበቁ ሰዎች የሚፏንኑበት እንዲሁም በፖለቲካ ቀረቤታቸው የቤተ ክርስቲያን ሳይሆኑ መቅደሷን የሚረመርሙ ሰዎች የሰለጠኑበት ዘመን መሆኑ ግን ያሳዝነናል። ሐዘን ብቻ ባይበቃም።

አቡነ ቶማስ አርፈዋል። ተተኪ ቶማስ እንዳይገኝ ግን የተዘራውን መልካም ዘር የሚያበላሹ ጥቃቅኑን ቀበሮዎች ማን አጥምዶ ይያዝልን? (መኃልይ 215) ሊቃውንት በወንበራቸው እንደተከበሩ እንዲኖሩ የሚያደርገው ማነው? ይህ ሁሉ ፀረ ሊቃውንት ሹመኛ ሌላ የተዋሕዶ አርበኛ የሆነ ቶማስ እንዳይፈጠር ተግቶ ሲለፋ ርቱዕ እምነት የያዘው ኦርቶዶክሳዊ የአቅሙን ለማድረግ የሚተባበርበት ዘመን መቼ ይቀርባል?
የብፁዕነታቸው በረከት ይደርብን፣
ጸሎታቸው ትድረሰን፤ አሜን
ቸር ወሬ ያሰማን።
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

abuna tomas 2(MKWebsite):- የምእራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ቶማስ ዐረፉ:: የቀድሞ ስማቸው አባ መዘምር ተገኝ የአሁኑ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ጥር 14 ቀን 1932 ዓ.ም ጎጃም ደጋ ዳሞት ዝቋላ አርባዕቱ እንስሳ ተወለዱ፡፡ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን በሚገባ ከተማሩ በኋላ ጸዋትወ ዜማን ከመሪጌታ አንዱዓለምና መሪጌታ ካሣ ይልማ ፣ ቅኔ ከመሪጌታ ፈንቴ /ዋሸራ/፣ መጻሕፍተ ሐዲሳትን ከመሪጌታ ብርሃኑ ወልደ ሥላሴ ፣ መጻሕፍተ ሊቃውንትን ከመሪጌታ ቢረሳ ደስታ ተምረዋል፡፡ በዘመናዊ ትምህርትም እስከ 6ኛ ክፍል ፣ የእንግሊዝኛን ቋንቋ በግላቸው የተማሩና የመኪና ጽሕፈት /type writing/ የሚያውቁ ነበሩ፡፡ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ዲቁና ከአቡነ ማርቆስ፣ ቅስና ከአቡነ ባልዮስ፣ ቁምስና ከብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖት ተቀብለዋል፡፡

በደብረ ሊባኖስ ገዳም መጻሕፍተ ሊቃውንትን ረዘም ላለ ጊዜ አስተምረዋል፡፡ በገዳሙ የሠራተኞች ቅርንጫፍ ማኅበር ሲቋቋምም የመጀመሪያው ሊቀ መንበር በመሆን አገልግለዋል፡፡ ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ተዛውረው በጎፋ መካነ ሕያዋን ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል በአስተዳዳሪነትና መጻሕፍተ ሓዲሳትንና ሊቃውንትን በማስተማር የሚጠበቅባቸውን ተልእኮ ተወጥተዋል፡፡ ጥር 14 ቀን 1972 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለሃይማኖት ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ አንብሮተ ዕድ ተሹመው ሰፊ አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ከዚያም ወደ አዲስ አበባ በመመለስ የታእካ ነገሥት በዓታ ለማርያምና መንበረ መንግሥት ግቢ ገብርኤል ገዳም የበላይ ጠባቂ ሆነው አገልግለዋል፡፡
ብፁዕነታቸው ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ የምእራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን ሲያገለግሉ ቆይተው፤ ባደረባቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መጋቢት 16 ቀን 2006 ዓ.ም መንበረ ጵጵስናቸው በሚገኝበት በፍኖተ ሠላም ከተማ ዐርፈዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸውም በዚያው በፍኖተ ሰላም እንደሚፈጸም ይጠበቃል፡፡
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]


(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 14/2006 ዓ.ም፤ ማርች 24/2014/ PDF በፍቅር ለይኩን):- ባለፈው ሳምንት ‹‹የፓትርያርኩ የለውጥ ተስፋዎች ወዴት ገቡ?›› በሚል አቶ መብራቱ መርሳ የተባሉ ግለሰብ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ን ፓትርያርክ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ በቤተ ክህነቱ ተቋም የተንሰራፋውን ሙሰኝነትንና ጎጠኝነትን በተመለከተ የተማፅኖ ጦማራቸውን በሪፖርተር ጋዜጣ በኩል ለቅዱስ ፓትርያርኩ ይደርስ ዘንድ አቅርበው ነበር፡፡ እኚህ ግለሰብም ባቀረቡት የተማፅኖ ደብዳቤያቸው ዋና አሳብም፣ ቅዱስ ፓትርያርኩ ከቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ውስጥ የነገሠውን አድር ባይነት፣ ዘረኝነት/ጎጠኝነትና ሙስና ለማጥፋት በአደባባይ ቃል የገቡበትን ዘመቻቸውን አጠንክረው እንዲቀጥሉበትና ፍሬውን በተግባር እንዲያሳዩ የሚጠይቅ ነው፡፡

በእርግጥ ይህ የአንድ ግለሰብ ብቻ ሳይሆን የበርካታዎች የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ መሪዎች፣ አባቶች፣ አገልጋዮችና ምእመናን የቀን ተሌት ብርቱ ምኞትና ተማፅኖ ነው፡፡ እኚህ ሰው ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ወደ ፕትርክና መንበር በመጡ ማግሥት የቤተ ክህነቱን ተቋም ከጎጠኞችና ከሙሰኞች ለማጥራት የገቡት ቃል ተግባራዊ ኾኖ ለማየት የነበራቸው ምኞት ከዓመት በኋላ የተጠበቀውን ያህል ዘመቻው ስኬት ባለማሳየቱና የለውጡም ሂደት በመንቀራፈፉ ሥጋት ቢጤ ገብቷቸው ይመስላል ይህን የተማፅኖ ደብዳቤ ለፓትርያርኩና ለሚመሩት የቤተ ክህነት ተቋም ለማድረስ የወደዱት፣ የተገደዱት፡፡
የእኚህ ግለሰብ ‹‹የለውጥ ያለኽ›› ተማፅኖ ጦማር በርካታዎችን የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶችን፣ አገልጋዮችንና ምእመናን የሚወክል እንደሆነ ነው በግሌ የማምነው፣ የምቀበለውም፡፡ የብዙዎች የአባት ያለኽ፣ የመሪ ያለኽ፣ የፍቅር ያለኽ፣ የእውነት ያለኽ፣ የፍትሕ ያለኽ፣ የበጎነት ያለኽ፣ የቅንነት ያለኽ፣ የመንፈሳዊነት ያለኽ፣ የለውጥ ንፋስ ያለኽ ጩኸትና አቤቱታ የቤተ ክህነቱን ተቋምና የአገሪቱን ሰማይ ክፉኛ ካደፈረሰው ሰንብቷል፣ ከራርሟልም፡፡
እውነተኛ የኾኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች፣ መንፈሳዊ መሪዎች፣ አገልጋዮችና ምእመናንም፣ አምላክ ሆይ ዝምታህ እስከ መቼ ነው?!፣ በቅዱስ መቅደስህ አደባባይ በትእቢትና በድፍረት እየተንጎማለሉ መሠውያህን በድሆች ዕንባና ደም የሞሉ ክፉዎችን የምትታገሳቸው እስከ መቼ ነው?!፣ በአፍቅሮተ ንዋይ አቅላቸውን የሳቱ፣ በክቡር ደምህ በዋጃኻቸው በጎችህ/በመንጋዎችህ ላይ በዋጋ የሚደራደሩ ይሁዳዎች- ምንደኞችና ነጋዴዎች ላይ የተግሣጽህ፣ የቁጣህ ጅራፍህ መቼ ነው የሚነሳው?!፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በዘርና በጎሳ የሚለያዩና የሚከፋፍሉ ዘረኞችና ጎጠኞችስ መቼ ነው ክፉ ዘራቸው የሚመክነው?!
የወንጌልን እውነት ቃል የሚሸቃቅጡ፣ መንፈሳዊ ሕይወትንና ስኬትን በግፍ በተከማቸ የዓመፃ ገንዘብና በዓለማዊ ሀብት የሚለኩ፣ የእግዚአብሔርን ስጦታ እንደ ስምኦን መሰሪ በገንዘብ ገዝተው በመቸርቸር ሀብትና ዝናቸውን ሰማይ ለማድረስ ዓውደ ምሕረቱን ያረከሱ አስመሳይ ነጋዴዎችና ምንደኞችስ ስለምን ቤትህን አጣበቡት?!፣ በቅድስናህ መቅደስ ላይ የሚዘባበቱ ፌዘኞችስ እስከ መቼ ሕዝብህን በሽንገላ ቃል ያባብሉታል፣ በክፉ ሥራቸውስ ያሰጨንቁታል፣ ያሰቃዩታል፣ ያስለቅሱታል?!
ስለ ሕዝብ መከራና ሰቆቃ፣ በየቀኑ እየፈራረሱ ስላሉ በክቡር ደምህ ስለዋጃኻቸው መቅደሶችህ/ሕዝበ ክርስቲያን ግድ የሚለውና በፈረሰው ቅጥር በኩል የሚቆም ነቢይ ኢሳይያስ ወዴት ይገኝ ይሆን?!፣ በመቅደስህ አጥር ስር ስለወደቁ የምድሪቱ ጎስቋሎችና መፃጉዎች፣ በረሃብ አለንጋ እየተገረፉ በቤተ መቅደስ ደጃፍ ስለሚያነቡ የዋኃን ሕፃናትና እናቶቻቸውስ ማን ነው ግድ የሚለው?!፣ ሕዝብህ በየቀኑ እየፈረሰ፣ እየተናደ ባለበት፣ የአንተን ቤት በዕብነ በረድና በከበሩ ድንጋዮች አንሠራለን፣ እነገነባለን የሚሉ ግብዞችንና ሙሰኞችንስ የሚገሥጻቸው ማን ይሆን?!
ነገሥታትንና መሪዎችን በአደባባይ የሚገጥሙ፣ ስለ ክፋታቸው፣ ኃጢአታቸውና በደላቸው ፊት ለፊት የሚገሥጹ፣ ስለ እውነትና ፍትሕ የሚቆሙ መንፈሳዊ ዐርበኛ የኾኑ ባህታውያን ዮሐንሶች ወዴት አሉ?!፣ ሕዝብን ከአስጨናቂው የፈረዖን አገዛዝ ነፃ የሚያወጡ፣ በሕዝባቸውና በወገናቸው ፍቅር የነደዱ የዘመናችን ሙሴዎችስ አድራሻቸው ወዴየት ነው?!፣ እንደ ነቢዩ ኤርምያስ ዕንባቸውን እያፈሰሱ ‹‹አቤቱ የኾነብንን አስብ፣ ስለ ቅዱስ ስምህ ስትልም ዘመናችን አድስ!›› የሚሉ ኤርምያሶችን ከወዴት እናገኝ ይሆን በማለት ብዙዎች በተማፅኖ ዕንባቸውን እንደ ራሄል ወደ ጸባዖት፣ ወደ አርያም እየረጩት ነው፡፡
ምድሪቱን በከደነው በዚህ ሁሉ ዋይታ፣ ጩኸትና ሰቆቃ መካከል እጅግ ወደ ተከበረው መንፈሳዊ መንበር፣ ሥልጣንና ኃላፊነት የመጡት ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ በሹመታቸው ማግሥት ሙሰኝነትንና ጎሰኝነትን አልታገሥም፡፡ ይህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ የልጆቻችን ብርቱ ጩኸትና ዋይታ ወደ ጆሮዬ ደርሷል እናም ጊዜው የለውጥ ነው፡፡ ከቅዱስ ሲኖዶስ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች፣ መንፈሳዊ አገልጋዮችና ልጆቻችን ጋር በመሆን ለለውጥ እንሠራለን፣ እንደክማለን በማለት የብዙዎችን ልብና ስሜት ከፍ አደርገውት ነበር፡፡ በዚሁ መንፈሳዊ ቆራጥነትና ትጋትም የተወሰዱ የብዙዎችን ልብ በተስፋና በሐሤት የሞሉ አንዳንድ የለውጥ ዕርምጃዎችም ነበሩ ማለት ይቻል ይመስለኛል፡፡
በመጀመሪያ ደረጃ ቅዱስ ፓትርያርኩ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተንሰራፋውን የጎጠኝነትና የሙሰኝነት ችግሮች መኖራቸውን አምነው መቀበላቸው አንድ የለውጥ ዕርምጃ ነው ማለት የሚቻል ይመስለኛል፡፡ ‹‹በቅጡ ተለይቶ የታወቀ ችግር በከፊል እንደተፈታ ይቆጠራል፡፡›› እንዲሉ፡፡ ሲቀጥልም ፓትርያርኩ እነዚህ ለበርካታ ዓመታት ሲንከባለሉ የቆዩ ችግሮችን በትክክል ለይቶ ከማስቀመጥና ባለፈም ተግባራዊ ዕርምጃዎችን በመውሰድ የለውጥ ዕርምጃው በአምላካችን ረዳትነት ፍሬ እንዲያፈራ እናደርጋለን በማለት እንቅስቃሴ መጀመራቸው ለብዙዎች ብሩሕ የለውጥ ተስፋን የፈነጠቀ ነበር ማለት ይቻላል፡፡
ለአብነትም ያህል ፓትርያርኩና ቅዱስ ሲኖዶሱ በበዓለ ሲመትና በሌሎች ክብረ በዓላት ሰበብ የሚወጣውን ከፍተኛ ወጪና የተንዛዛ ድግስና ውዳሴዎች እንዲቀሩ ማድረጋቸው፣ በድግስ ሰበብና በበዓላት ሽርጉድ ኪሳቸውን የሚያደልቡ ሙሰኞችን በሩ እንዲዘጋባቸው አድርጓል፡፡ በዚህም በውድ ስጦታዎችና ገጸ በረከቶች ሰበብ፣ እጅ የመጠመዘዝ ያህል ድብቅ አጀንዳቸውንና ፍላጎታቸውን ለማስፈጸም የሚተጉና የሚሯሯጡ አስመሳዮችና ሙሰኞችም ቀኑ እንዲጨልምባቸው ኾኗል፡፡
ሌላውና በተለይም በግንባር ቀደምትነት ሊጠቀስ የሚገባው የለውጥ እንቅስቃሴ ደግሞ በቤተ ክህነቱ አስተዳደር ሥራ ውስጥ ግልፅነትና ተጠያቂነት ያለበት፣ መንፈሳዊ ትጋት፣ በጎነትና ቅንነት የሚንጸባረቅበት ሙያዊ/ፕሮፌሽናል አሠራር እንዲኖርና ለማድረግ ከመነጋገር አንስቶ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ልጆችና ምሁራን የተሳተፉበት ‹‹የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መዋቅር አደረጃጀትና የአሠራር መመሪያ ጥናት›› ሰነድ ቀርቦ ሰፋ ያለ ተከታታይ ውይይቶች የተደረገበት የዛን ሰሞኑ ቅዱስ ሲኖዶስ፣ የቤተ ክህነቱ የአስተዳደር ሠራተኞችና መንፈሳዊ አባቶች የተሳተፉበት ጉባኤ በዋናነት የሚጠቀስ ነው፡፡
ይህን የለውጥ ትግበራ ጥናት ሰነድን ያዘጋጀው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ነው፡፡ ይህ ዳጎስ ያለ ጥናትም በቁጥር ጥቂት የማይባሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች የኾኑ ምሁራንና ባለሙያዎች የተሳተፉበትና በገንዘብ ሲሰላም ቤተ ክርስቲያኒቱን በመቶ ሺኅዎች የሚገመት ወጪን ከማውጣት የታደጋት በብዙ ድካምና በብርቱ ጥንቃቄ የተዘጋጀ የጥናት ሰነድ እንደሆነ ነው አብዝቶ የተነገረለት፡፡
በዚህ የጥናት ሰነድ ላይም በየደረጃው ተከታታይ የኾኑና ውጤታማ ነበሩ ሊባሉ የሚችሉ ውይይቶች ተደርጎባቸዋል፡፡ ይሁን እንጂ በጉባኤው ላይ ይህን የመዋቅር አደረጃጀትና የአሠራር ጥናት ሰነድ በምን መልኩ ሥራ ላይ ልናውለው እንችላለን የሚለው ላይ በተነሡ አንዳንድ ልዩነቶችና አለመግባባቶች የተነሳ የተለያዩ ቡድኖች ጎራ ለይተው የቃላት ጦር ሲማዘዙ፣ ሲጠዛጠዙ ታዝበናል፡፡ አሁንም የቃላት ጦርነቱ፣ መወራረፉና መጎነታተሉ እንደቀጠለ ነው፡፡ በአንፃሩም ችግሩንና ቀውሱን ከቤተ ክህነቱ ክልል በማውጣት በስውርም ኾነ በግልጽ እየታየ ያለ ሌላ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መሠረት ያለው ጠንካራ ግፊት እንዳለ የሚከራከሩ ድምፆች ደግሞ እዚህም እዛም እየተሰሙ ናቸው፡፡
ለቤተ ክርስቲያኒቱ የሚቆረቆሩ፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገራት ባሉ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ዩኒቨርሲቲዎች የተማሩ ምሁራንን በሥሩ አሳባስቦ የያዘው ማህበረ ቅዱሳን ለዚህ የለውጥ ዕርምጃ የበኩሉን ዕገዛና ጥረት ለማድረግ ደፋ ቀና ቢልም፣ ማኅበሩ ያቀረበው የዳጎሰ የጥናት ሰነድ ሁሉንም የቤተ ክርስቲያኒቱን መሪዎችና አባቶች ባስማማ መልኩ ተቀባይነት አግኝቶ የለውጥ ትግበራውን ዕውን ለማድረግ ዕንቅፋት እንደገጠመው ግን በግልጽ እየተስተዋለ ነው፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ይህ የጥናት ሰነዱ ብቻ ሳይሆን ሌሎች ተዛማጅ የኾኑ እንቅስቃሴዎቹም ከሰሞኑን እክል እንደገጠማቸው ሰምተናል፣ ታዝበናልም፡፡ ለአብነትም የአብነት መምህራንን በተመለከተ የጠራው አገር አቀፍ ጉባኤ መታገዱ የሰሞኑን በርካታዎችን ያሳዘነ ዜና ሆነ ማለፉን ልብ ይሏል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ቅዱስ ፓትርያርኩ ከሰሞኑን፣ ‹‹ቤተ ክርስቲያን በባይሎጂና በኬምስትሪ ምሩቃን አትመራም፡፡›› የሚለው መረርና ከረር ያለ ውስጠ ወይራ ንግግራቸው በማኅበሩ ማንነትና አቋም ላይ ያነጣጠረና ጥርጣሬያቸውንም ገሃድ ያወጣ ንግግር እንደሆነ ነው ብዙዎች ሲናገሩ የተደመጡት፡፡
የኾኖ ኾኖ ፓትርያርኩ በአደባባይ ያወጁትንና ቃል የገቡለትን ቤተ ክህነቱን ተቋም ከሙሰኞችና ከጎጠኞች እናጻዳለን ዘመቻቸውም ኾነ ለዚሁ የለውጥ ዘመቻ ያግዛል በሚል በማኅበረ ቅዱሳን ያቀረበው የጥናት ሰነድ የመጨረሻው ዕጣ ፈንታ ምን ይኾናል የሚለውን በእርግጠኝነት ለመናገር ግን አሁንም በትዕግሥት መጠበቅ የሚያስፈልግ ነው የሚሉ በርካታ ታዛቢዎች አልጠፉም፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የቤተ ክህነቱ ተቋም ትልቁና ዋንኛ ችግሩ የሚጀምረው ከላይ ከመንፈሳዊ መሪዎቹ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች አካባቢ መንፈሳዊ ሕይወትና መንፈሳዊ ቆራጥነት/ቅንዓት መጥፋቱ በቤተ ክህነቱ ተቋም ለተከሰተው የዚህ ሁሉ ምስቅልቅልና ቀውስ ዋንኛው ምክንያት እንደኾነ አድርገው ያቀርባሉ፡፡ በከፋ የሞራል ውድቀትና ዝቅጠት ውስጠ የተዘፈቁ፣ ምድራዊ ሀብትና ዝና የሚያንኾልላቸው፣ የለየላቸው ሙሰኞችና ጎሰኞች ከላይ እስከ ታች በተሰገሰጉበት የቤተ ክህነቱ ተቋም ውስጥ ለውጥን ለማምጣት መንገዱ አልጋ በአልጋ ይኾናል ተብሎ አይታሰብም፣ አይጠበቅምም፡፡
ላለፉት በርካታ ዓመታት ሲንከባለል የቆየ ይህ የተወሳሰበው የቤተ ክህነቱ ተቋም ችግሮች በአንድ ጀምበር ይፈታሉ ብሎ ማሰብም የዋኽነት ነው፡፡ እናም ለውጡን ዕውን ለማድረግ ከሚያስፈልገው ትዕግሥትና ቁርጠኝነት ባሻገር የክርስትና ሃይማኖት ዓምድና መሠረት የኾኑት ፍቅር፣ በጎ ሕሊና፣ ቅንነትና ታማኝት እንዲኖሩ የግድ ይላል፡፡ መሰሪነት፣ አድር ባይነት፣ አጎብዳጅነትና ግብዝነት በነገሡበትና መንፈሳዊነት ፈፅሞ እየተሰደደበት ባለበት ተቋም ውስጥ ለቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ መሪዎችና አባቶች ፍቅርና ኅብረት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ህልውና፣ የመንፈስ አንድነትና ሰላም ቀዳሚና ዋና አጀንዳ ሊኾን በተገባው ነበር፡፡
ከሁሉም በፊት ፍቅርንና መንፈሳዊ አንድነትን ለማምጣት ፈቃድም ኾነ አቅም ያነሰው የቤተ ክህነቱ ተቋም ጋሪውን ከፈረሱ በማስቀደም ጉልበቱንና አቅሙን በከንቱ እያባከነ ነው በማለት የሚተቹ ብዙዎች ናቸው፡፡ የቤተ ክህነቱ ተቋምም ኾነ መሪዎች በእውነትም ሊያሳስባቸውና ሊያስጨንቃቸው የሚገባው ቀዳሚው ጉዳይ የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ አንድነትና ሰላም መሆን ነበረበት፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ መሪዎችና አባቶች ወይም የቤተ ክህነቱ ተቋም ወሳኝና ቀዳሚ አጀንዳ የአንድ ሰሞን ብቻ ወሬና ግርግር ኾኖ ማለፉና አሁን አሁን ደግሞ ከእነ መፈጠሩም የመረሳቱ ነገር ለመኾኑ መቅደም ያለበት የትኛው ነው ‹‹ሰላምና አንድነት ወይስ …›› የሚል ጥያቄን በተደጋጋሚ እያስነሳ ነው፡፡
ይህ የቤተ ክርስቲያኒቱ የአንድነትና የሰላም ጉዳይ የሚያሳስባቸው በርካታዎችም የፓትርያርኩም ኾነ የቤተ ክህነቱ ተቋም የለውጥ እንቅስቃሴ የቤቱ መሠረት ተነቃንቆ እያለ ጣርያውና ግድግዳው እንዳይፈረስ ከሚታገል የዋኽ ሰው ጋር በማመሳሰል የሚያቀርቡ ታዛቢዎች አልጠፉም፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ ኾኖ በማያውቅ ለሦስት ተከፍላ፣ የኢትዮጵያ ሲኖዶስ፣ ሕጋዊው ሲኖዶስ፣ ገለልተኛ በሚል የተለያዩ፣ የተከፋፈሉና ተገለባባጭና አድር ባይ የኾኑ ፖለቲከኞች እንደሻቸው የሚጠመዙዟቸው አባቶች ልዩነታቸውን በሰላም ፈተው ወደ አንድነት መምጣት እስካልፈቀዱ ድረስ፣ ለቤተ ክህነቱ የምንመኘው እውነተኛውና ተግባራዊው ለውጥ ህልም ነው ሲሉ አጥብቀው ይከራከራሉ፡፡ ዛሬ ከዳር እስከ ዳር መነጋገሪያ የኾነው ሙሰኝነትም ኾነ ጎጠኝነት የቤተ ክህነቱ ለገባበት ቀውስና የሞራል ውድቀት አንድ ወይም ጥቂቱ መገለጫ እንጂ የቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረታዊ ችግር ጥልቅ፣ የተወሳሰበና ዕድሜ ጠገብ ነው፡፡ መፍትሔውም ፍቅር፣ አንድነትና ሰላም ግድ የሚላቸው፣ ለእግዚአብሔርና ለቤቱ መንፈሳዊ ቅንአት ያላቸው መንፈሳዊ መሪዎች እንዲኖሩና እንዲበዙ መጸለይና መሥራት ነው፡፡  
የፓትርያርክ አቡነ ማቲያስ ሙሰኞችንና ጎጠኞችን የማጥራት ዘመቻው ፍሬያማ እንዲኾንና ለዚሁ የለውጥ ዘመቻ ትግበራም ያግዛል ተብሎ በቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች/ምሁራን የቀረበው የጥናት ሰነድ ተግባራዊ ውጤት እንዲያመጣ ከተፈለገ መቅደም ያለበት አማራጭ ይህ ነው ሲሉም ይናገራሉ፡፡ ስለሆነም ይላሉ እነዚህ አስተያየት ሰጪዎች፣ የቤተ ክህነቱ ተቋም ማስቀደም ያለበት ዋነኛው ዕርምጃ መሆን ያለበት መንፈሳዊነትን ያስቀደሙ የእግዚአብሔርና የቤቱ ቅናት የሚያቃጥላቸው፣ መመሪያቸውና መለያቸው ፍቅር የኾነ፣ ሰላምንና ዕርቅን የሚሰብኩ፣ ለእውነትና ለፍትሕ የቆሙና የሚከራከሩ መሪዎችና አባቶች እንዲኖሩና እንዲበዙ መሥራትና መትጋት የግድ ይላል በማለት አስተያየታቸውን ይሰነዝራሉ፡፡
እነዚህ ትችቶች፣ መከራከሪያዎችና አስተያየቶች እንዳሉ ኾነው ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ የጀመሩት የቤተ ክህነቱን ተቋም ከሙሰኞችና ከጎጠኞች የማፅዳት ዘመቻቸውን አጥብቀው እንዲገፉበት የሚመኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች፣ አገልጋዮችና ምእመናን ድምፅ አሁንም ጎልቶ እየተሰማ ነው፡፡ በመጨረሻ አንድ ነገር ለማለት እወዳለኹ፡፡ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በፕትርክና ዘመናቸው የተከፋፈለችውን ቤተ ክርስቲያን አንድነት በማስጠበቅ፣ የቤተ ክህነቱን ተቋም ከሙሰኞች፣ ከአስመሳዮችና ከጎጠኞች የፀዳች በማድረግ አዲስ ታሪክ ያስመዘግቡ ዘንድ ልባዊ ምኞቴ ነው፡፡
Deje Selam is a venue of news, views and opinions about or related to the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church. [email protected]

(ደጀ
ሰላም፤ ሚያዚያ 10/2005 ዓ.ም፤ ኤፕሪል 18/2013/ READ IN PDF)፦ እንደምን ሰነበታችሁ፣ እንደምን ከረማችሁ። ልክ በወራችን ብቅ አልን።
በዚህ አንድ ወር ውስጥ እ

                                               www.globalallianceforethiopia.org

     &nbsp…

ቤተ ክህነቱ ይህንን ያደረገው ዕርቁ የፈረሰው በውጪዎቹ ችግር
መሆኑን ለማጠየቅ ነው፤
የደጀ ሰላም ምንጮች “ቤተ ክህነታዊ ሐረካት” ብለውታል። 

(ደጀ ሰላም፤ የካቲት 26/2005 ዓ.ም፤ ማርች 5/2013/ PDF)፦ ይህ ጽሑፍ “ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ወእጬጌ ዘመንበረ

(Mahibere Kidusan/ የካቲት 24/2005 ዓ.ም፤ ማርች
3/2013)፦ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ
ቤተ ክርስቲያን 6ኛ ፓትርያርክ ሆነው የተመረጡት የብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያ

(REPORTER):- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስድስተኛው ፓትርያርክ ሆነው ባለፈው ሐሙስ የተመረጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በውጭ አገር …

በስደት ላይ የሚገኘው ሲኖዶስ ሢመት ፕትርክናውን አውግዟል
‹‹ዕርቀ ሰላሙ ቅዱስ ሲኖዶስ በተናገረው መሠረት ይቀጥላል›› /ተመራጩ ፓትርያርክ/

(ADDIS A…

አዎን፤ አቡነ ማትያስ 6ኛ ፓትርያርክ ሆነዋል

     ደጀ ሰላም እያካሄደች ባለችው
መደበኛ ያልሆነ “የድረገጽ” ድምጽ አሰጣጥ አቡነ ማቴዎስ ብዙ …

    ደጀ ሰላም እያካሄደች ባለችው
“የድረገጽ” ድምጽ አሰጣጥ አቡነ ማቴዎስ ቅድሚያውን ይዘዋል፤

(ደጀ
ሰላም፤ የካቲት 21/2005 ዓ.ም፤ ፌብሩዋሪ 28/201…

(MK Website/  PDF http://bit.ly/YwKqd1):-የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 6ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ
በዝግጅት ላይ እንደምትገኝ ይታወቃል፡፡ በ

(ደጀ
ሰላም፤ የካቲት 18/2005 ዓ.ም፤ ፌብሩዋሪ 25/2013/ PDF)፦ ቅዳሜ የካቲት 16/2005 ዓ.ም ቀርበው በአብዛኛው የቅ/ሲኖዶስ አባላት ይሁንታ አግኝተዋል የተባሉት
አስም…

(ደጀ
ሰላም፤ የካቲት 16/2005 ዓ.ም፤ ፌብሩዋሪ 23/2013/ PDF)፦ የስድስተኛው  ፓትርያርክ 
አስመራጭ   ኮሚቴ  በዛሬው   ዕለት  የዕጩዎቹን 

‹ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያንና
ለቤተ ክርስቲያን ብለው ብቻ ማሰብ፣ ይገባቸዋል›› – (ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል)

(አዲስአድማስ ጋዜጣ፤ የካቲ…

(ደጀ ሰላም፤ የካቲት 13/2005 ዓ.ም፤ ፌብሩዋሪ 20/2013/ PDF)፦ በአባቶች
መካከል የተፈጠረውን መለያየት ላማራቅና ዕርቅ ለማውረድ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ የቆየው የ

ይህ ጽሑፍ የአቅማቸውን ጥቂት ነገር ለማድረግ የሚተጉትን ላይመለከት ይችላል።

(ደጀ ሰላም የካቲት 8/2005፤
ፌብሩዋሪ 15/2012/ PDF)፦ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአ

(መልዕክተ ተዋሕዶ – ዘሮኪ በተለይ ለደጀ ሰላም
እንደጻፉት/ PDF)፦ ደጀ ሰላማውያን እንደምን ሰነበታችሁ? ብዬ መጠየቅ፥ ዛሬ አልፈለኩም። እንዴት እንደሰነበ

(Reporter Amharic):- የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቅርስ፣ የባህልና የመገናኛ ብዙኅን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሰሜን የአገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ የአገሪቱ ቅርሶችን እ

·       “የትግራይ ክልል ተወላጅ ካልሆናችሁ በዚህ ገዳም መኖር አትችሉም”
ተብለናል፤

·       “ከቅርብ
ጊዜ ወዲ

(ደጀ
ሰላም፤ ጥር 12/2005 ዓ.ም፤ ጃኑዋሪ 20/2013/ PDF)፦ ቅዱስ
ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱ ምዕራፍ 4 ቁጥር 5 ላይ ያለውን “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖ

4ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ
ስለ በዓለ ጥምቀት እና ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ያስተላለፉት መልእክት:: 

Deje Selam is a venue of…

(ደጀ
ሰላም፤ ጥር 11/2005 ዓ.ም፤ ጃኑዋሪ 19/2013/ PDF)፦ በትናንትናው ዕለት የአሜሪካው ሲኖዶስ  ያወጣው መግለጫ የተለያዩ ጉዳዮችን የያዘ ነበር፡፡ እነዚህም …

(ወልደ  አረጋዊ፤ በተለይ ለደጀ ሰላም እንደጻፉት/ PDF)፦ ሕይወት ጣፋጭም መራራም ጽዋዋን ደጋግማ ትግታለች፡፡ ዛሬ ረቡዕ ሰው፣ ብሎም ኢትዮጵያዊ የኦርቶ…

(ደጀ ሰላም፤ ጥር 8/2005፤ ጃኑዋሪ 16/2013/ PDF) በጉጉት
ሲጠበቅ የነበረውና ከመነሻውም በውጪ ተጽዕኖ ሥር የወደቀው የቅ/ሲኖዶስ ጉባኤ እንደተፈራውም ዕርቀ ሰላሙ…