ብፁዕ አቡነ ቶማስ የሃይማኖት ገበሬ አርፈዋል? ተተኪው ቶማስ ከየት ይገኛል?
(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 19/2006 ዓ.ም፤ ማርች 28/2014/ PDF)፦ በዚህ የዘመነ ብላ ተባላ፣ ጸረ ሊቃውንት እና መፍቀሬ ተሐድሶ ዘመን በቤተ ክህነት ከቁንጮው እስከ ግርጌው ባሉ በልቶ አደሮች ሲገፉ ከኖሩት አባቶች መካከል አንዱ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ነበሩ። አፈር ይቅለላቸው። ዕረፍታቸው እጅግ ቢያሳዝነንም ማንም ከዚያ ስለማይቀር የምንጸጸትበት አይደለም። እንዲህ የተማሩ ሊቃውንት እንደ ተርታ ሰው ወደጎን ተገፍተው ዳዊት ባልደገመ አፋቸው ነገረ ቤተ ክርስቲያንን የሚዘነጥሉ፣ ንብረቷን የሚዘርፉ፣ አሰረ ክህነታቸውን ያልጠበቁ ሰዎች የሚፏንኑበት እንዲሁም በፖለቲካ ቀረቤታቸው የቤተ ክርስቲያን ሳይሆኑ መቅደሷን የሚረመርሙ ሰዎች የሰለጠኑበት ዘመን መሆኑ ግን ያሳዝነናል። ሐዘን ብቻ ባይበቃም።
አቡነ ቶማስ አርፈዋል። ተተኪ ቶማስ እንዳይገኝ ግን የተዘራውን መልካም ዘር የሚያበላሹ ጥቃቅኑን ቀበሮዎች ማን አጥምዶ ይያዝልን? (መኃልይ 2፥15) ሊቃውንት በወንበራቸው እንደተከበሩ እንዲኖሩ የሚያደርገው ማነው? ይህ ሁሉ ፀረ ሊቃውንት ሹመኛ ሌላ የተዋሕዶ አርበኛ የሆነ ቶማስ እንዳይፈጠር ተግቶ ሲለፋ ርቱዕ እምነት የያዘው ኦርቶዶክሳዊ የአቅሙን ለማድረግ የሚተባበርበት ዘመን መቼ ይቀርባል?
የብፁዕነታቸው በረከት ይደርብን፣
ጸሎታቸው ትድረሰን፤ አሜን
ቸር ወሬ ያሰማን።
