“አይቴ ሀለዉ ቀደምት ጳጳሳት”?
(ደጀ ሰላም፣ መጋቢት 20/2006 ዓ.ም፤ ማርች 29/2014/ PDF)፦ ሥርዓተ ቅዳሴውን ለመምራት ተሰይመው ለተመለከታቸው ከረጅሙ ነጭ ጽህማቸው ጋር ውብ የሆነውን መረዋ ድምጽ ሲሰማ ምድራዊ ሳይሆን ከሰማይ የተገለጠ መልአክ ይመስሉ ነበር፡፡ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት የተለየ ፍቅር ስለነበራቸው በተጋበዙበት መድረክ ሁሉ አክብረው በሰዓቱ ይገኛሉ፡፡ ለማስተማር ከተነሱም በትርጋሜ የተዋዛ ምስጢር አዘል ትምህርታቸውን ለምእመናን ቀምመው ያቀርባሉ፡፡ ለሃይማኖት ያላቸውን ቀናዊነት ለመረዳት በትምህርታቸው መግቢያ የሚናገሩትን መልእክት መስማት ብቻ በቂ ነው፡፡ ይህ የመግቢያ መልእክታቸው ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ያልተበረዘች ያልተከለሰች መሆኛን የሚስረዱበት በተለያዩ ዘመናት የተነሱባትን መናፍቃን በመጥቀስ እነዚህ ሁሉ ያልበረዛት ያልከለሳት መሆናን የሚገልጹበት ነው፡፡ እናም በጥዑም አንደበታቸው ስለቤተ ክርስቲያን ሲናገሩ ለሰማቸው የሊቃውንቱ ዘመን የእነ እትናቴዎስ ዘመን የሃይማኖት ቅናት በውስጣቸው እንዳለ ይረዳል፡፡ ብፁዕ አቡነ ቶማስ፡፡
በደብረ ሊባኖስ ገዳም መጻሕፍተ ሊቃውንትን ረዘም ላለ ጊዜ በማስተማር ቆይተው ነው ወደ አዲስ አበባ የተዛወሩት፡፡ በገዳሙ ውስጥ ሲኖሩ የነበራቸውን መንፈሳዊ ሕይወት እና አንድምታውን የማስተማር ብቃት በወቅቱ የነበሩ አባቶች የሚመሰክሩት በታላቅ አድናቆት ነው፡፡ ሊቅነትን ከመንፈሳዊነት ጋር ይዘው በመገኘታቸውም ቤተ ክርስቲያን ለበለጠው አላፊነት አጭታ ለጵጵስና ማዕረግ በቅተዋል፡፡ መናፍቃንን በተመለከተ ግልጽ የሆነ ቀጥ ያለ አቃም ነበራቸው፡፡ፀረ ማርያም የሆነን የተሐድሶ ጭፍራ መታገሥ አይችሉም፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የነበረውን የተሐድሶ እንቅስቃሴ ሥሩን ነቅለው የጣሉበት የዲንነት ዘመናቸው ለዚህ ምስክር ነው፡፡ እንደእነ ቅዱስ ቄርሎስ የመናፍቃን መቀጥቀጫ መዶሻ ነበሩ፡፡ የኋላ ኋላ ይህ ቀናዒነታቸው እና አድርባይ ሊሆኑ ያለመቻላቸው ጉዳይ በቤተ ክህነቱ ውስጥ በተሰገሰጉ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ስላልተወደደላቸው እንዲጠሉና እንዲገለሉ አድርጓቸዋል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ምርጥ ምርጡን ለወዳጆቼ በሚሉበት እንዳሻቸው ሃገረ ስብከት በሚያድሉበትም ዘመን አቃማቸውን ብዙም ስሎማይወዱላቸው ጠረፋማ ሥፍራዎች ላይ እንዲመደቡ ሆነዋል፡፡ለነገሩ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ስለሚመደቡበት ሃገረ ስብከት ብዙም የሚጨነቁ ስላልሆኑ ወደተላኩበት ሁሉ በደስታ ይሄዳሉ፡፡ ፍሬም ያፈራሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሰው ያለህ በምትልበት በዚህ ወቅት እንዲህ ያለ አባት ማጣት ትልቅ ሀዘን ነው፡፡ ብፁዕነታቸው ወደ አገለገሉት አምልክ በክብር ቢሄዱም እኛ ግን በትልቁ ተጎድተናል፡፡
ወቅቱ በአጠገባችን ያሉ ጥቂት መንፈሳዊ አባቶችን በስስት የምንመለከትብት ነው፡፡ “አይቴ ሀለዉ ቀደምት ጳጳሳት፤ የቀደሙ አባቶች ደጋጎቹ ሊቃነ ጳጳሳት ወዴት አሉ?” እያልን ዘመን ገድባቸው የተለዩንን በሀዘንና በቁጭት የምናስታውስበት ነው፡፡ በግል ቂምና በቀል ቤተ ክርስቲያንን ለመናፍቃን አሳልፈው የማይሰጡ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚገባቸውን መከራ ሁሉ በጥብዓት የሚቀበሉ፣ ከአላውያን ነገሥታት እምነት የለሽ መንግሥታት ጋር የማይዛመዱ፣ በፍልስፍናና በምድራዊ ተድላ ተይዘው በእምነት ጉዳይ ቸልተኛ ያልሆኑ፣ መስሎ ለማደር ሲሉ ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጋር የማይተባበሩ፤ በሚያልፍ ጊዜ የማያልፍ የታሪክ ጠባሳ ለትውልዱ ላለመተው የሚጠነቀቁ፤ እኔ ካልተነካሁ ሕዝቡም ሆነ አገልጋዩ ያሻውን መከራ ቢቀበል ምን አግብቶኝ ሲሉ የማይገኙ አባቶችን ተጠምተናል፡፡
እንደ ሙሴ ሕዝብህ ከሚጠፋ እኔን ከሕይወት መጽሐፍ ደምስስ የሚሉ፣ እንደ ነቢዩ ኤልያስ ስለ እግዚብሔር ክብር የሚቀኑ፣ እንደ ነቢዩ ዳዊት የተቀመጡበት ዙፋን የሚኖሩት የተድላ ኑሮ የተነሱበትን የማያዘናጋቸው፤ በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ኃላፊያትና መጻዕያትን የሚረዱ፣ ሳይነገራቸው የመናፍቃንና የአላውያን ነገሥታት የጥፋት አካሄድ የሚገባቸው፡፡ እንደ ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔር በክብሩ ዙፋን ተቀምጦ የሚታያቸው፣ ከምድራዊ ነገሥታት ከመዘመድ ይልቅ አደራውን ለሰጣቸው ለሰማዩ ንጉሥ መታዘዝ እንደሚበልጥ የሚረዱ፡፡ እንደ ሐዋርያት እስከ ሞት የሚታመኑ፡፡ እንደ ሊቃውንት መናፍቃንን የሚገስጹ፣ አልመለስ ያሉትንም የሚያወግዙ አባቶችን ተጠምተናል፡፡
የቤተ ክርስቲያን አምላክ ነገን እንደ አትናቴዎስ ያለ አትናቴዎስ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን የሚተካ ሌላ አባ ጊዮርጊስ እንዲተካ አጥብቀን እንለምነው፡፡ ለእርሱ ምን ይሳነዋል? ይህ ሁሉ ወጀብ አልፎ ደግ ዘመን ያመጣልን ይሆናል፡፡ ለሁሉም በሕይወት ያሉትን ለተዋሕዶ ጠበቃና አርበኛ የሆኑ አባቶች ዕድሜ ያርዝምልን፡፡ ያረፉትን አባቶች በረከትም በያለንበት ያድለን፡፡ አሜን፡፡ ቸር ወሬ ያሰማን፤ አሜን። ቸር ወሬ ያሰማን።
