PDF
“ጋዜጠኝነትን እና የፖለቲካ ድርጅትን ሽፋን በማድረግ የሀገሪቱንና የሕዝቦቿን ሰላም ለማደፍረስ ከሚያስቡና ከሚፈልጉ ‘ሀይላት’ ጋር ግንኙነት በማድረግ የተለያዩ የሽብር ተግባራትን ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ በቁጥጥር ስር አውለናቸዋል።“
ይህ መግለጫ (መልስ) የኢትዮጵያ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 ከወጣበት ከነሀሴ 2001 ዓ.ም. ጀምሮ ጋዜጠኞችና በሰላማዊ መንገድ ተመዝግበው የፖለቲካ ምህዳሩን የተቀላቀሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት በኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ከታሰሩ በኋላ በመንግስት አካላት የሚሰጥ የተለመደ አባባል ነው። የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ እስከ መስከረም 2007 ዓ.ም ባሉት አምስት ዓመታት ውስጥም ከጋዜጠኛ እስከ ፖለቲከኛ (political personalities)፣ ከሀይማኖት መሪዎች እስከ ጦማሪያን፣ ከታጣቂ ወታደሮች እስከ የኮንትሮባንድ ነጋዴዎች… በዚሁ አዋጅ አማካኝነት ‘ሽብርተኝነታቸው ተረጋግጦላቸዋል’ ወይም ‘ይረጋገጥባቸው ዘንድ ፍርዳቸውን እየጠበቁ ይገኛሉ።’ ለመሆኑ ይህ ከ14 ዓመት ህፃን[1] እስከ 80 ዓመት አዛውንት[2] በሽብርተኝነት ወንጀል ክስ የሚያስቀጣው፣ ይህ ከጉምቱ ምሁራን እስከ ገበሬዎች ድረስ የሚያስረው… ሕግ በተጨባጭ ስፋትና ጥበቱ ምን ያህል ይሆን? ለታሪካዊ ጥያቄዎች ያለው ምልከታስ? በሀገሪቱ ስላለው የዲሞክራሲ ሁኔታስ (The state of Democracy) ምን ይነግረናል? ስለ ጨቅላው የኢትዮጵያ ፌደራሊዝምስ ከፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ ተግባራዊነት አንፃር ምን ይታየናል? ወ.ዘ.ተ. የሚሉትን ጥያቄዎች መሰረት በማድረግ በመሬት ላይ ያሉ የሕጉ እውነታዎችን በመመርመር (Fact investigation) ምልከታዎቹን (Implications) በዚህ ፅሁፍ ለማየት ሞክረናል።
የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ
ዓለማቀፉ የፀረ-ሽብር ውጊያ (The Global War on Terror) በቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ቡሽ <We will not tire, we will not falter> ንግግር ከታወጀ ጀምሮ በተለያዩ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚገኙ ሀገሮች በሽብርተኝነት ዙሪያ ያላቸውን የሕግ ማዕቀፍ ለማሻሻል ጥረት ማድረግ ጀመሩ። ኢትዮጵያም የዓለማቀፉ የፀረ-ሽብር እንቅስቃሴ አካል መሆን አለብኝ በማለት እንዲሁም ሽብርተኝነት በኢትዮጵያ ላይ ግልፅ እና ድርስ አደጋ (clear and present danger) ደቅኗል በሚል መነሻ የፀረ-ሽብር ሕግ አርቅቃ ለፓርላማ አቀረበች።
ረቂቁ በቀረበበት ወቅት የተለያዩ አካላት (የፓርላማ አባላት፣ የሰብአዊ መብት ተቋማት፣ ጋዜጠኞችና የጋዜጠኛ ማኅበራት ወ.ዘ.ተ.) ረቂቅ ሕጉ ሰፊ የሽብርተኝነት ድርጊት ትርጉም ይዟል፣ ‘ማወቅ ሲገባው’፣ ‘አድርገው ይረዱታል ተብሎ ሊገመት የሚችል መልዕክት’ የመሳሰሉት የሚሉ ለትርጉም ክፍት የሆኑ የወንጀል አይነቶችን አካቷል፣ ለፖሊስና ለደህንነት አካላት እጅግ የተለጠጠ ስልጣን ይሰጣል፣ እንደ የዋስትና መብት ያሉ የዜጎችን ሕገ-መንግስታዊ መብቶች ይነፍጋል፣ የሥነ ስርዓት እና የማስረጃ ሕጎችን በማቅለል ወንጀለኝነትን የማስረዳት ሸክምን ከዓቃቤ ሕግ ወደ ተጠርጣሪ ግለሰቦች ያሸጋግራል (shifting burden of proof) ወ.ዘ.ተ. የሚሉ ትችቶችን ቢያቀርቡም፤ ‘እነዚህን የሕጉን ክፍተቶች የተለያዩ የመንግስት አካላት ላልተገባ ጉዳይ ሊያውሏቸው ይችላሉ’፣ ‘ተቃውሞን እና የመናገር ነፃነትን ወደ ወንጀልነት ያሸጋግራል’ የሚሉ ስጋቶችን በጊዜው ቢያነሱም ሕጉ በፓርላማ ከመፅደቅ ያገደው ነገር አልነበረም።
በሕጉ ዙሪያ የሚቀርቡ ብዙና የተለያዩ ትችቶች ቢኖሩም ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው የዚህ ፅሁፍ ዓላማ የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ በተጨባጭ የትኞቹን የሕብረተሰብ ክፍሎች እያጠቃ ነው? ስለ አጠቃላይ የሀገሪቱ ሁኔታስ ምን ያመለክተናል? የሚሉትን ጉዳዮችን መዳሰስን ዓላማ ያደረገ ነው።
(ማስታወሻ: – በዚህ ፅሁፍ ውስጥ የሚጠቀሱ ተከሳሾች በአሁኑ ወቅት በጊዜያዊ ቀጠሮ ወይም ክስ ተመስርቶባቸው በመደበኛ ቀጠሮ ላይ ያሉ ናቸው።)
የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ አተገባበር
የፀረ- ሽብርተኝነት ሕጉ ከመውጣቱ በፊት እንዲሁም ከወጣ በኋላ የሚቀርቡበትን ትችቶች የመንግስት አካላት ምላሽ ሲሰጡበት: –
“ሕጉን ቃል በቃል የገለበጥነው ከAmerican Patriotic Act እንዲሁም ከእንግሊዙ የTerrorism Act ነው። እኛ ጋር ሲመጣ ለምን ትችት እንደሚቀርብበት ሊገባን አልቻለም።” የሚል ነው። መንግስት እውን ቃል በቃል ገልብጦታልን? የሚለውን ጥያቄ ለመረዳት እንችል ዘንድ የአንዲት እንግሊዛዊት እና የአንድ አሜሪካዊ ታሪክን በማቅረብና በማነፃፀር ትግበራው ላይ ፍተሻ እናድርግ።
እንግሊዛዊቱ Kate Kaplan በዩኒቨርሲቲ ቆይታዋ Mathematicsን በMajorነት Computer Scienceን ደግሞ Minor በማድረግ ትምህርቷን የጨረሰች ስትሆን፤ በተለያዩ መስሪያ ቤቶችም ከምረቃዋ በኋላ በስራ ዓለም ያሳለፈች ናት። በስራ ዓለምም በData Expertነት Specialize አድርጋለች። ከስራዋ ጎን ለጎን ደግሞ የተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም እንደርሷ ሁሉ ለሀገራቸው መሻሻል የሚተጉ ጓደኞችን ለማፍራት የቻለች ሲሆን፤ ከእነዚህ ወዳጆቿ ጋር በመሆንም በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ የምትጦምር ነች። ንባቧን እና ግንዛቤዋን ለማዳበር ይረዳት ዘንድም በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ የተፃፉ ፅሁፎችን ከድረ-ገፆች ላይ በመገልበጥ ታነባለች። በIreland Republic ዙሪያ ጥያቄ ያለውን IRA የተባለ ፓርቲ ፕሮግራምም ለማንበብ Laptop ላይ ገልብጣ አስቀምጣለች። በዚህ ሁኔታ ላይ እያለች የእንግሊዝ የፀጥታ አካላት እርሷንና የማኅበራዊ ሚዲያ ጓደኞቿን ሰብስቦ ያሰራቸው ሲሆን ‘የሽብርተኝነት ተግባራትን ሊፈፅሙ ሲሉ ያዝኳቸው’ በማለት ክስ መስርቶባቸዋል። የክሱ ማስረጃ ሁነው ከቀረቡ ሰነዶችም አንዱ Kate ግንዛቤ ለማግኘት በማሰብ ከድረ-ገፅ የገለበጠችው እና ማንም ሰው በድረ-ገፁ አድራሻ ገብቶ ሊያነበው የሚችለው የIRA የፖለቲካ ፕሮግራም ነው። Kateና ጓደኞቿም ፍርዳቸውን እየተጠባበቁ ይገኛሉ። የእንግሊዝ Terrorism Act ደግሞ የተወነጀሉበት አዋጅ ነው።
በተመሳሳይ ሁኔታ Andrew Martin በአሜሪካው New York University የእንግሊዘኛ ቋንቋ መምህር ሲሆን ከስራው ጎን ለጎን ደግሞ የDemocratic Party የአመራር ክበብ ውስጥ ተሳትፎ አለው። ከፖለቲቻ ስራው ጋር በተያያዘም የተለያዩ ሰነዶችን የሚያገላብጥ ሲሆን ከእነዚህ ሰነዶች አንዱ ደግሞ ስለ አሜሪካው Black Panters Party የሚገልፅ ሰነድ ነው። በስልጣን ላይ የነበረው የRepublican Party Andrewን ከሽብርተኛ ድርጅት ከሆነው Black Panters Party ጋር ግንኙነት አለው በማለት አሳስሮ የአምስት ዓመት ፍርድ ፈርዶበት በአሁን ሰዓት እስሩን እየገፋ ይገኛል። የRepublican መንግስት በአቶ Andrew ላይ ፍርድ የበየነበት የAmerican Patriotic Act አንቀፆችን በመጠቀም ነው።
እነዚህን ሁለት ጉዳዮች የጠቀስነው የኢትዮጵያ መንግስት የፀረ-ሽብርተኝነት ህጉን ቃል በቃል ገለበጥኩባቸው የሚላቸው ሀገሮች አሜሪካና እንግሊዝ የሽብርተኝነት ክሶች እስከምን ድረስ ይደርሳሉ? የሚለውን ጉዳይ ለማየት ሳይሆን ሕጉ ቃል በቃል ተገለበጠ በተባለባቸው ሀገሮች የኢትዮጵያ መንግስት በአሁኑ ሰዓት የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን እየተጠቀመበት ባለው አግባብ ቢጠቀሙ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ለማሳየት ሲባል፣ በአሁኑ ወቅት በሽብርተኝነት ወንጀል ተከሳ በቃሊቲ የምትገኘውን ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁንን በKate Kaplan፣ እንዲሁም በፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ ተከሶ አምስት ዓመት ተፈርዶበት እስሩን እየገፋ የሚገኘው መምህር በቀለ ገርባን በAndrew Martin በመተካት ማህሌት እና በቀለ ላይ እየሆነ ያለው ነገር የኢትዮጵያ መንግስት ‘ምዕራባውያንም ተመሳሳይ የህግ ማዕቀፍ ነው ያላቸው’ በማለት እያቀረበው ያለውን ማስተባበያ ምን ያህል በአተገባበሩ የተሳሳተ እንደሆነ በቀላሉ ያሳያል።
ጦማርያን እና ሰላማዊ ፖለቲከኞችን በመፃፋቸው እና ለሀገራቸው መልካም ነገርን በማሰብ ፖለቲካ ውስጥ የገቡ ግለሰቦችን የሚያስር – የሚከሰው የፀረ-ሽብርተኝነት ሕግ በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ እንጂ በሌላ ዓለም ማግኘት ከባድ ነው። Kateና Andrew ‘ሽብርተኛ’ የሚባሉት በኢትዮጵያ እንጂ በአሜሪካ ወይም በእንግሊዝ ተመሳሳይ ሁኔታ ሊፈጠር አይችልም፡፡ ታዲያ ቃል በቃል ከምዕራቡ ዓለም የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጎች ‘የተገለበጠው’ የኢትዮጵያ የፀረ-ሽብርተኝነት ሕግ እንዴት ቢሰራ ነው ሁሉንም የሕይወት መስመሮች ‘በሽብርተኝነት’ ሊፈርጅ የቻለው?
“የሽብርተኛ ፍለጋና ምርመራው ሂደት “
የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ በተግባር እንዴት ነው እየሰራ ያለው? የሚለውን ጥያቄ መመለሳችን ከላይ የጠየቅነውን ቀዳሚ ጥያቄ ይመልስልናል። እንዲህ በአጭር ምሳሌ እንመልከት:-
‘ሀሰን፣ ሀያት እና ከድር በፖሊስ (በደህንነት ኃይል) ከሽብርተኝነት ጋር የተገናኘ ወንጀል ሊፈፅሙ ሲሉ ተያዙ’ ተብለው ታሰሩ። አሰራሩ እንዲህ ይቀጥላል:-
- በብሔራዊ የመረጃና የደህንነት ኃይል በቁጥጥር ስር ይውላሉ። በተለያዩ የደህንነት ‘እስር ቤቶች’ ላልተወሰነ ጊዜ (ከ6 ወር በላይ በደህንነት ቢሮ የቆዩ ሰዎች አሉ) ከከፍተኛ ድብደባ እና ስቃይ ጋር ይቆያሉ። በአብዛኛው ፍርድ ቤትም ሆነ ቤተሰብ ያሉበትን ሁኔታ አያውቅም።
- በደህንነት ‘እስር ቤቶች’ የነበራቸውን የፈተና (ordeal) ጊዜ ከጨረሱ በኋላ ለፌደራል ፖሊስ ተላልፈው ይሰጣሉ። የፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ዘርፍ (ማዕከላዊ) ‘ማረፊያ ቤት’ በማረፍም ‘የምርመራ’ ጊዜያቸውን ይጀምራሉ። የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ባለው ‘የፀረ-ሽብር ዲቪዚዮን’ አማካኝነት ባሉት ከ20 በላይ መርማሪዎችም ‘ምርመራው’ ይጀመራል። በዚህ የምርመራ ወቅትም እጅግ ኢሰብአዊ የሆኑ ድርጊቶች ይፈፀምባቸዋል። የተጠረጠሩበትን ‘የሽብርተኝነት ድርጊት’ እስኪያምኑ ድረስም መከራና ስቃያቸው ይቀጥላል። በዚህ ሁኔታ እስከ አራት ወራት ለሚቆይ ጊዜ ይቆያሉ (እስከ ስምንት ወራት በማዕከላዊ የቆዩ ሰዎች አሉ)።
- በአብዛኛው ‘የሽብርተኝነት ወንጀል ፋይሎች’ ላይ እንደሚታየው በነሀሰን፣ ሀያት እና ከድር ጉዳይ ላይም ፖሊሲ በቂ ማስረጃ ስለማይኖረው ‘ማስረጃ’ እዛው በወንጀል ምርመራ ዘርፍ መርማሪዎች ይዘጋጃል። እንዴት?
ሀ. ድብደባና ስቃዩን በማጠናከር ከሶስቱ ተከሳሾች አንዱን (ለምሳሌ ከድርን) በጓደኞቹ በሀሰን እና በሀያት ላይ ምስክር እንዲሆን (Accomplice witness) በማስገደድ ፖሊስ የሰው ማስረጃ ይፈጥራል። ከድርም ከክሱ ይወጣል።
ለ. ፖሊስ የፈለገውን ቃል በመፃፉ ሀስን እና ሀያት እንዲፈርሙ ያስገድዳቸዋል። ቃላቸውንም ‘በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ስርዓት ሕግ አንቀፅ 27(2) መሰረት በነፃ የተሰጠ’ ይለያል።
ሐ. ምናልባትም ሀሰን እና ሀያት ‘ቃላችንን በድብደባ ያለፈቃዳችን ነው የሰጠነው’ በማለት በፍርድ ቤት በክሱ ሒደት ወቅት እንዳያስተባብሉት ፖሊስ ስጋት ካደረበት እዛው በወንጀል ምርመራ ዘርፍ ማረፊያ ቤት (ማዕከላዊ) እያሉ ወደ ፍርድ ቤት በመውሰድ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ስርዓት ሕጉ አንቀፅ 35 መሰረት ‘አሸባሪነታቸውን’ አምነው ቃላቸውን እንዲሰጡ ያስደርጋል። በፍርድ ቤት የካዱ እንደሆነ ወደ ማረፊያ ቤት ሲመለሱ ሌሊቱን ሙሉ ከባድ ስቃይ ይጠብቃቸዋል።
መ. ካስፈለገም ‘የሀሰት ምስክሮችን ያሰለጥናል’፣ የወንጀል የሀሰት ሰነዶችን ያዘጋጃል። ወ.ዘ.ተ.
- ፖሊስ ‘ምርመራውን’ በዚህ መንገድ ካጠናቀቀ በኋላ ምርመራውን ለፍትህ ሚኒስትር ይልካል። የፍትህ ሚኒስትርም አስፈላጊውን ‘ፖለቲካዊ ግምገማ’ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ካደረገ በኋላ አራት አቃብያን ሕጎችን (አቶ ብርሃኑ ወንድማገኝ፣ አቶ ቴዎድሮስ ጌታቸው፣ አቶ ዘውዱ በቀለንና አቶ ሰውበሰው አድማሱን) ላቀፈው የፀረ-ሽብርተኝነት case team ያስተላልፋል። አቃብያነ ሕጎቹም የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ ላይ ከተደነገጉት አስር (10) ወንጀሎች በአንዱ ወይም ከዛ በላይ ክስ ያቀርባሉ።
- በመጨረሻም የሀሰንና የሀያት ጉዳይ ወደ ፍርድ ቤት ይቀርባል። አቃቤ ሕግ ከድርን የሰው ማስረጃ አድርጎ ያቀርባል። የሀሰንና የሀያትን ለፖሊስ ወይም ለስር ፍርድቤት ተገደው የሰጡትን የተከሳሽነት ቃል በሰነድ ማስረጃነት ያቀርባል። የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ እና 19ኛ ወንጀል ችሎቶች ካሏቸው ዳኞች[4] ሶስቱ በጉዳዩ ላይ ይሰየሙና ፍርድ ይሰጣሉ። ከድር ምስክር በመሆን ነፃ ይወጣል። ሀሰንና ሀያት ደግሞ ‘አሸባሪነታቸው’ ተረጋግጦባቸው ይፈረድባቸዋል። (በነገራችን ላይ አሁን ባለው አሰራር የፍርድ ሂደቱ ከሁለት ዓመት በላይ ጊዜ ሊወስድ ይችላል)
ይህ ‘የሁሉም’ ለማለት በሚያስደፍር መልኩ በፀረ-ሽብርተኝነት ሕግ መሰረት የተከሰሱ ሰዎች ጉዳይ አካሄድ ነው። በዚህም መንገድ ዜጎች ከማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ገለል እንዲሉ ይደረጋሉ። ምክንያቱም እነሱ ‘ኢትዮጵያዊ አሸባሪዎች’ ናቸውና። የእነዚህን ኢትዮጵያውያን አሸባሪዎች ማንነት ማወቃችን የሽብርተኝነት ትግሉን ምንነት እና የሀገሪቱን ጉዞ በጉልህ ያሳየናልና እስኪ ፍተሻ እናድርግ።
‘መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ፌደራሊዝም’
“ደርግ በወደቀበት ሰዓት በሀገሪቱ አስራ ሰባት (17) የሚሆኑ የታጠቁ ሀይላት ነበሩ። ይህም ዜጎች በደርግ ስርዓት የተከፉ ምን ያህል ወገኖች እንደነበሩ አመላካች ነው።” በማለት ኢህአዴግ ስልጣኑን ከደርግ በተረከበበት ወቅት የነበረውን ሁኔታ በተደጋጋሚ ያስረዳል።
ኢህአዴግ አያይዞም የተለያዩ ቡድኖችን መከፋትና ብሶት ለመቀነስና እስከ መጨረሻውም ለማስወገድ የፌደራል ስርዓት እንዲዘረጋ፤ ይህ የፌደራል ስርዓትም ‘ሀገሪቱን እንደ ዩጎዝላቪያ ከመሆን የታደጋት ፍቱን መድኃኒት’ እንደሆነ ይገልፃል።
ደርግም ከወደቀ ሩብ ምዕተ ዓመት እየሆነው ነው፤ የኢትዮጵያም የፌደራል ስርዓት ሀያኛ ዓመቱን ይዟል። እውን ከላይ የተጠቀሱት እውነታዎች ምን ያህል መሻሻል አሳይተዋል? የፌደራል ስርአቱስ ከቃላት ባለፈ ምን ያህል እውነተኛ ለውጥ አምጥቷል? የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን እና ሕጉ ተግባራዊ የሆነባቸውን ቡድኖች ማንነት ማየቱ ለጥያቄዎቻችን መልስ ለመስጠት ይሆናልና እስኪ እንመልከት።
በአሁኑ ወቅት ገዥውን ስርዓት ለመገዳደር በማሰብ ‘ፋኖነትን’ የመረጡ ቡድኖች የደርግ ጨካኝና አምባገነን ስርዓት ሲወድቅ ከነበሩት የታጠቁ ሀይሎች ቢበልጡ እንጂ አያንሱም። የአሁኖቹን ታጣቂዎች ከደርግ ወቅቶቹ የሚለያቸው፣ የአሁኖቹ ‘በአሸባሪነት’ የተፈረጁ መሆናቸውን ነው።
ይህ ፅሁፍ በተፃፈበት ወቅት ክስ ተመስርቶባቸው በቀጠሮ ላይ የሚገኙ አስር የተለያዩ የክስ መዝገቦችን ብናይ መልሳችን ግልፅ ይሆንልናል።
“የጋምቤላ ክልል አሁን ባለው የፌደራል ስርዓት ምንም ዓይነት ጥቅም እያገኘ አይደለም። ለዚህም መፍትሄው ስርዓቱን በኃይል ማስወገድ ነው።” በሚል መነሻ አምስት (5) የተለያዩ ቡድኖች መሳሪያ አንስተዋል። ከነዚህም አምስት (5) ፓርቲዎች መካከልም በአቶ ሙድ ጎይባሬ የሚመራው የጋምቤላ ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) ጋር በተገናኘ 11 ሰዎች ማለትም
- ኡቺሚ አፐይ ኡቻላ
- ኡማን ኡድሉቻም
- ኡቻን ኡድላ ኦፒዮ
- ኡመድ ኡጁሉ ኡማን
- ኝበዲ ኡባንግ ኡጃቶ
- ኦፒዮ ቹር ኡባንግ
- ኡመድ ኡቶ ኡማን
- ኡፐዶካ ኡቱን ኝግየው
- ታደሰ ኡዱጊ ቲፋ
- ኡማን ኡካይ ኡኩችና
- ኦኬሎ ኡበር ኡቻን
በፌ/ዓ/ህ/መ/ቁ 322/06 በቀን 18/07/06 በፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀፅ 3 (1, 2 እና 3) መሰረት ክስ ተመስርቶባቸዋል፤ ጋህነንም የሽብርተኛ ድርጅት እንደሆነ በክሱ ተመልክቷል። ከጋምቤላ ሳንወጣ አሁን በቅርቡ ደግሞ በቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዝዳንት በአቶ ኦኬሎ አኳይ ኡቻላ እንደሚመራ በክሱ ከተመለከተው የጋምቤላ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ጋዴን) አባላት ናችሁ ተብለው የተከሰሱ ሰባት ግለሰቦችን እናገኛለን። እነርሱም
- ኦኬሎ አኳይ ኡቻላ
- ዴቪድ ኡጅሉ ኡባንግ
- ኡቻን ኦፒዮ ኡሞድ
- ኡማን ኝክየው ኡድሉ
- ኡጅሉ ቻሞ ኡኮይ
- ኦታካ ኡዋር ኡጋላና
- ኡባንግ ኡመድ አቦላ ናቸው።
በቀን 04/10/2006 ዓ.ም. በፌ/አ/ህ/መ/ቁ 508/06 በቀረበባቸው በዚህ ክስ ጋዴን የሽብርተኛ ድርጅት እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን ክሱም በፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀፅ 4 ላይ የተዘረዘሩትን ተግባራት በመተላለፍ እንደሆነ ተገልጿል።
እስኪ ወደ ሌላ ክልል እንለፍ። በኮለኔል አለበል አማረ እንደሚመራ የሚነገርለትን የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሀይሎች ህብረትን (አዴሀህ) እናገኛለን። የፌደራል አቃቢ ሕግ በመዝገብ ቁጥር 071/06 በቀን 28/12/05 ባቀረበው ክስ ‘ግንቦት ሰባት ከተባለ አሸባሪ ድርጅት ጋር ግንኙነት ፈጥሮ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ኦዴሀህ የተባለ ‘ሽብርተኛ ድርጅት’ ጋር አባል በመሆን ሲንቀሳቀሱ ያዝኳቸው’ ያላቸውን 10 ሰዎች በፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀፅ 7(1) መሰረት ከሶ እናገኛለን። ግለሰቦቹም
- ማስረሻ ታፈረ ወ/ገብርኤል
- ሻለቃ አለምነው አየለ ነጋሽ
- ብርቁ አዲሱ ውቡ
- ታደሰ መንግስቱ በላይ
- የፀዳው ካሴ አሉላ
- አወቀ ደስታው ምህረቴ
- መሀመድ ግዛቸው ፋንታው
- ቴዎድሮስ ሀይሌ
- ታደሰ በለጠ
- ታደሰ ባዩ ገበየሁ ናቸው።
ወደ ኦሮሚያ ክልል ተጉዘናል። ባለፉት 20 ዓመታት የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባላት ናችሁ በሚል እጅግ በጣም ብዙ ኦሮሞዎች ታስረዋል፣ ተሰደዋል ወይም ተገድለዋል። ይህ ሁኔታ አሁንም በሰፊው ቀጥሏል። የአሁኑን ለየት የሚያደርገው ክሱ ‘ራሱን ኦነግ ብሎ ከሚጠራው ‘ፀረ-ሰላም’ ሀይል ውስጥ አባል በመሆን…’ ከሚለው የተለመደ የክስ ቃል በተለየ መንገድ ‘ራሱን ኦነግ ብሎ ከሚጠራው ‘አሸባሪ’ ድርጅት ውስጥ አባል በመሆን…’ ወደሚል መቀየሩ ብቻ ነው። ምስጋና ለፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ ይሁንና። ለዚህም ጥሩ ማሳያ ይሆኑን ዘንድ ሁለት የአቃቢ ሕግ መዝገቦችን እንጠቅሳለን።
በ22/07/2006 ዓ.ም. በፌ/ዓ/ሕግ/መ/ቁ 376/06 በመሰረተው ክስ
- ደልዴሳ ዋቆ ጃርሶ
- ገልገሎ ጉዮ ቦሩ
- ዋርዮ ጣጤሳ ጉዮ
የተባሉ ግለሰቦች የኦነግ አባል በመሆን ‘የሽብርተኝነት ድርጊቶችን’ ሲፈፅሙ ይዣቸዋለሁ’ በማለት የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን አንቀፅ 3(1 እና 2) እንዲሁም አንቀፅ 7(1) በመጥቀስ ክስ መስርቷል። በተመሳሳይ ሁኔታ የፌደራል ዓቃቢ ሕግ በቀን 11/2006 ባቀረበው ‘የሽብር ወንጀል’ ክስ የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የነበሩት
- አብዲ ከማል የሱፍና
- ቶፊቅ ረሽድ ዩያ
‘የአሸባሪው’ ድርጅት የኦነግ አባላት በመሆን የሽብር ተግባራትን ልትፈፅሙ ስትሉ ተይዛችኋል’ ተብለው የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀፅ 7(1) ተጠቅሶባቸው ክሳቸውን በማረፊያ ቤት ሆነው እየተከታተሉ ይገኛሉ። በ2006 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል በነበረው አለመረጋጋት ምክንያት ከተለያዩ የክልሉ ዩኒቨርስቲዎች (ከሀሮማያ፣ ከጅማ፣ ከወለጋ… ዩኒቨርስቲዎች) የተያዙ ተማሪዎች እንዲሁም ከተለያዩ የክልሉ አካባቢዎች (ከወለጋ፣ ከሞያሌ ወ.ዘ.ተ.)ተይዘው የታሰሩ ዜጎች በኦነግነት ተጠርጥረው በፌደራል የወንጀል ምርመራ ዘርፍ (ማዕከላዊ) የሚገኙ ሲሆን ይህ ፅሁፍ እስከተፃፈበት ቀን ድረስም ክስ ሳይመሰረትባቸው ከአራት ወራት ለሚበልጥ ጊዜ በወንጀል ምርመራ ዘርፍ ‘ማረፊያ ቤት’ ውስጥ ይገኛሉ።
በድጋሚ ወደ ሀገሪቱ የምዕራብ ጫፍ እንጓዝ፤ ‘አሸባሪው’ ቤሕነንን እናገኛለን – የቤንሻንጉል ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ። በአቶ አብዱል ወሀብ መሀዲ የሚመራው ቤሕነን “የክልሉ ነዋሪዎች ኢህአዴግ ከዘረጋው ስርዓት ተጠቃሚ ሊሆኑ አልቻሉም። መፍትሔውም ስርዓትቱን በሀይል ማስወገድ ነው።” በሚል መነሻ ነፍጥ ያነገበ ፓርቲ ነው። በፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ ‘የሽብርተኛ ድርጅት’ ከመባል ግን አልተረፈም። የፌደራል አቃቢ ሕግ በ19/12/2006 ዓ.ም. ባቀረበው ክስ
- አብዱልከሪም አብዱሰመድ አብዱልቃድር
- ሀዎጃ ሚነሳ አጉር
- ኢላቅ ኢብራሒም ዓሊ (ዕድሜ 17)
- አዴላ ጃባለ ንምር
- አብዲ ሀሚዝ ፈረንሳ
- ፋተልሙላ አጣሂር አከሶ
የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁን አንቀፅ 7(1) በመጥቀስ ከላይ የተዘረዘሩትን ስድስት ግለሰቦች ‘የአሸባሪው የቤሕነን አባል ናችሁ በማለት ክስ አቅርቦባቸዋል።
ሰሜን ኢትዮጵያ ጫፉ ላይ ነን። በስልጣን ላይ የሚገኘው ‘ኢህአዴግ’ ትግሉን የጀመረበት የትግራይ ክልል ውስጥ። ‘ገዢው ስርዓት ለትግራይ ሕዝብ አመጣልሃለሁ ያለውን ዴሞክራሲና ፍትህ ማምጣት አልቻለምና ስልጣን በቃው’ በማለት የተነሳው ዴሞክራሲያዊ ሕዝቢ ምንቅሳቀስ ትግራይ (ዴሕምት) ደግሞ ከትግራይ ክልል የተገኘው ‘አሸባሪ’ ድርጅት ነው። የፌደራል ዓቃቢ ሕግ በ
- ብሎፅ ገ/ፃድቃን
- ነጋሌ ብርሃኑ
- ሹማይ ተበጀ
ላይ ባቀረበው ክስ ‘የአሸባሪው’ ዴሕምት አባል በመሆን የተለያዩ የሽብር ተግባራትን ሊፈፅሙ ሲሉ ይዣቸዋለሁ በማለት የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን አንቀፅ 7(1) በመጥቀስ ክስ መስርቶባቸዋል።
በዘጠኙም የፌደራል ክልሎች ‘አሸባሪ’ ድርጅቶችን መፈለጋችንን ቀጥለናል፤ ማረፊያችንም ኦጋዴንያ ሆኗል። የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀፅ 25 መሰረት በሽብርተኛ ድርጅትነት ከሰየማቸው 5 ድርጅቶች ውስጥ ላለፉት ሶስት አስርት ዓመታት ኦጋዴንን ነፃ ለማውጣት እየታገለ የሚገኘው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) አንዱ ሲሆን፤ የፌደራል አቃቢ ሕግም በየጊዜው ‘የአሸባሪው’ የኦብነግ አባላት ናችሁ በማለት እጅግ ብዙ ክሶችን በኦጋዴን ተወላጆች ላይ የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን በመጥቀስ ክስ አቅርቦ ‘ፍርዳቸውን’ በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።