የሰማያዊ አቅጣጫ ስህተትና የማይጠቅም ነው – ግርማ ካሳ
አቶ እያስፔድ ተስፋዬ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የሥራ አስፈጻሚ አባልና የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ ናቸው። “አቧራን ለማጥራት – ነጻነት ለምርጫ ቅድመ ሁኔታ ነው” በሚል ርእስ አንጹ ጽሁፍ አቅርበዋል። በሚከተለው ሊንክ ያገኙታል። የእኝህ ወጣት አቀራረብ በጣም ተመችቶኛል። በነጻነት ነጥባቸውን በማስቀመጥ ለምርጫ ከመገባቱ በፊት መሟላት ያለበት ቅድመ ሁኔታ እንዳለ ይከራከራሉ።
viewtopic.php?f=2&t=90558
የድርጅት አባል ባልሆነም፣ የምደገፈው ድርጅት አለ። እርሱም የአንድነት ፓርቲ ነው። ይህ ፓርቲ፣ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ለምርጫ እንደሚሳተፍ በይፋ ለህዝብ አሳዉቆ፣ «2007 ለለውጥ»፣ «ተደራጅ ለምርጫ» በሚል መርህዎች በአገሪቷ ሁሉ መጠነ ሰፊ የምርጫ እንቅስቃሴ ጀመሯል።
የአንድነት አቋም ለምን ትክክለኛ እንደሆነ፣ በአንጻሩም ደግሞ የሰማያዊ ፓርቲ አቋም ለምን የወቅቱን ሁኔታ ያላመዛዘነ የተሳሳተና በ እወቀት ሳይሆን በስሜት ላይ የተመሰረተ አቋም እንደሆነ ለማሳየት እሞክራለሁ። የአንድነት አባል እንዳለመሆኔ፣ ከዚህ በታች የምጽፈው የግል አስተያየቴ እንደሆነ ከወዲሁ ለአንባቢያን አሳውቃለሁ።
ብዙዎቻችን በምርጫ በመግባትና ባለመግባት ዙሪያ የሚደረገው ዉይይት አካል ሆነን ሐሳቦችን ሰንዝረናል። አሁን ባለው ሁኔታ ምርጫ መገባት የለበትም የሚሉ ወገኖች ፣ ከምን ተነስተው እንደዚያ እንደሚሉ እረዳለሁ። ሆኖም የነርሱን አቋም ተቃዉሜ ስጽፍ፣ ምርጫ ባለመግባት የሚገኝን ጥቅም ሊያሳዩን ባለመቻላቸው ነው።
እዚህ ዉጭ አገር ያሉ አንዳንድ በጠመንጃ ትግል እናምናለን የሚሉ ቡድኖች፣ ምርጫ እንዲገባ አይፈልጉም። (እነርሱ ዉጊያቸውን ትተው ለምን በሰላማዊ ታጋዮች ዙሪያ እንደሚጨነቁ ባይገባኝም) ምናልባት ምርጫ ከተደረገና አንጻራዊ መሻሻል ከመጣ የነርሱ ፖለቲካ ዜሮ ስለሚገባ ሊሆን ይችላል ምርጫዉን የሚቃወሙት። በመሆኑም ከነዚህ ቡድኖች በምርጫ ዘመቻ ላይ ተቃውሞ ቢሰማ ልንገረም አይገባም።
አገር ቤት በሰላም የሚታገሉ ወገኖች ግን ፣ ምርጫዉን ቦይኮት ሲያደርጉ ፣ በተመሳሳይ ሁኔታ ደርጅታቸውን ወይንም ሕዝቡን የሚጠቅም መሆኑን በማስላት መወሰን ያለባቸው መሰለኝ። ይሄን ካደረጉ የቦይኮት ጥሪው ችግር ይኖረዋል ብዬ አላስብም። ነገር ግን ትንሽ ያልተመቸኝ ፣ እነ አቶ እስያስፔድ እንዲያስረዱን የምፈልገው ፣ ቦይኮት ማድረጉ ምን ጥቅም ለትግሉም ሆነ ለሰማያዊ ፓርቲ እንደሚያስገኝ ነው። ቦይኮት ተደረገ፤ ከዚያስ ? ? ትልቅ መመለስ ያለበት ጥያቄ።
እስከሚገባኝ ድረስ የሰማያዊ ፓርቲ ሆነ ትብብር በቀዳሚነት አቋማቸው በግልጽ አይታወቅም። አንዳንድ አመራሮች ያለ ቅድመ ሁኔታ ወደ ምርጫው እንገባለን ይላሉ። አንዳንዶቹ ደግሞ ተቃራኒዉን ይናገራሉ። ስለዚህ በቅድሚያ የሰማያዊም ሆነ ትብብሩ አቋም ግልጽ መሆን አለበት። አንድ የአመራር አባል ፌስ ቡክ ላይ በመጻፉ ሳይሆን፣ ደርጅቶቹ በኦፊሴል ለሕዝብ አቋማቸዉን ግልጽ ማድረግ አለባቸው።
ለዉይይት ያህል.፣ ቅድመ ሁኔታ ሳይሟላ ወደ ምርጫው አይገባም ከተባለ፣ ቀጣዩ ጥያቄ የሚሆነው ቅድመ ሁኔታዎቹ ምንድን ናቸው የሚል ነው። ከዚያ ገዚው ፓርቲ ቅድመ ሁኔታዎችን እንዲያሟላ ምን እየተደረገ ነው ? የተደረገውስ ምን ዉጤት አመጣ ? የሚሉ ጥያቄዎች ይነሳሉ።
የሰማያዊ ፓርቲ አገዛዙ ቅድመ ሁኔታዎችን እንዲያሟላ፣ ጫና ለማድረግ የአንድ ወር መርሃ ግብር አጠናቋል። ዉጤቱን ሁላችንም የምናወቀው ነው። ካለፈው የአንድ ወር መርሃ ግብር የተለየ ነገር በሚቀጥሉት መርሃ ግብሮች ምን ሊፈጠር እንደሚችል በርግጠኝነት መናገር ቢያስቸግረም፣ መገመቱ ግን ይከበዳል ብዬ አላስብም።
የሰማያዊ ፓርቲ ቅድመ ሁኔታዎች አልተሟሉም ብሎ ከምርጫው ቢወጣ፣ ገዢው ፓርቲ የሚፈራው ወይም የሚጎዳበት ሁኔታ የሚፈጥር ቢሆን ኖሮ «ቦይኮት አደርጋለሁ» በሚል ማስፈራራትና ቅድመ ሁኔታዎች ማስቀመጥ ያስኬዳል ብዬ ልቀበል እችል ነበር። ሆኖም ያደረች ባቄላ እንደሚባል፣ ገዢው ፓርቲ ሰማያዊ ምርጫ ዉስጥ ገባ፣ አልገባ ግድ አይሰጠዉም። የሰማያዊ ምርጫውን አለመሳተፍ ለነርሱ ኢንሲግኒፊካንት ነው። በመሆኑም ምርጫ አንገባም ማለት ፖለቲካ ፋይዳ አይኖረዉም።
ሌላው ቦይኮት በሚደረግበት ጊዜ ፣ ሕዝቡም ቦይኮት እንዲያደርግ ማስተባበር ያስፈልጋል። ህዝቡ ወደ ምርጫ ሄዶ ፣ ሰማያዊ ግን ብቻዋን ቦይኮት ቢያደረግ፣ እንደ ቢራቢሮ አየር ላይ የሚንሳፈፍ ድርጅት ነው የሚሆነው። ድርጅቶች በሙሉ ተባብረው፣ ተነጋግረው፣ በተቀናጀ መልኩ ቦይኮት እንዲደረግ ዘመቻ ቢያደርጉ፣ ህዝቡም የቦይኮቱ አካል እንዲሆን ቢያደራጁ፣ ከቦይኮቱ ጎን ለጎን ሰላማዊ ሰልፎችን የሥራ ማቆም አድማዎችን ቢጠሩ …ቦይኮት ሊሰራ ይችላል። ከዚያ ዉጭ ግን ቦይኮት የሚያመጣዉ አንዳች ፋይዳ አይኖርም። (እስከሚገባኝ ድረስ የሰማያዊ ፓርቲ ከነ አንድነት ፓርቲ ጋር አብሮ መስራቱ እንደ አለርጂክ እየሆነበት ነው። ከተመሰረቱ ጊዜ ጀመሮ ከአንድነት ጋር ፉክክር እንጂ የያዙት፣ በቁም ነገር፣ «በአንድ ላይ መሰባሰባች የአገርና የሕዝብ ጥያቄ ነዉ» በሚል ሂሳብ ለመንቀሳቀስ ሲሞክሩ አይታዩም)
በመጨረሻ የማነሳው ነጥብ የፕራክቲካሊቲ ነጥብ ነው። ሰማያዊ «አገዛዙ ላይ ጫና አሳድሬ፣ ቅድመ ሁኔታዎች እንዲሟሉ አደርጋለሁ» ይላል። በአራት ወራት ጊዜ ዉስጥ ምን ያህ ይሄ ግብ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል ? እዉነት እንነጋገርና በአራት ወራት ዉስጥ አገዛዙ ምርጫ ቦርድን ይለውጣልን ? ለነዚህ ጥያቄዎች መልሱ « አይችልም፣ አይሆንም» የሚል ነው።
ምርጫ ቦርድ ላይ በየምርጫ ጣቢያ ጫና ሊያደረግ የሚችለዉን ህዝብ፣ ድምጹን እንዲያስከበር ከማደራጀትና በየሜዳው ሄዶ ከመንቀሳቀስ ዉጭ ሌላ አማራጭ አይኖርም። የሰላማዊ ትግል ሰራዊት ሕዝቡ ነው። ወታደሮች ከኋላው ያላሰለፈ ጀነራል የትም እንደማይደርስ፣ ህዝቡን ከበስተኋላ ያላሰፈ የሰላማዊ ትግል መሪም ሆነ ድርጅት ሩጫ ከንቱ ነው።
«አንድነት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በምርጫው እሳተፋለሁ» ብሎ መግለጫ መስጠቱን አልቃወምም፡፡ አባላቶቼን ከወዲሁ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ይረዳኛል ብሎ ይሆናልና፡፡ ልክ እንደዚሁም ሁሉ ሌላውም የእኛን አቋም እንዲያከብርልን እሻለሁ፡፡» ሲሉም አቶ እያስፔድ ጽሁፋቸውን ያጠቃልላሉ። በመርህ ደረጃ ትክክል ናቸው። ሆኖም በዚህ ወሳኝ ወቅት የሰማያዊና የአንድነት ስትራቴጂዎች የተለያዩ በመሆናቸው ሕዝቡን የማደናገር ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል። አንድነት በአንድ በኩል ለምርጫ ተመዝገቡ እያለ ለምርጫ ሲቀሰቀስ፣ ሰማያዊ ደግሞ በሌላ በኩል ቦይኮት ይደረግ እያለ የሚቀሰቅስ ከሆነ፣ በተቃራኒ ወገን ቆሙ ማለት ነው። የግድ አንድነቶች የሰማያዊ አማራጭ ትክክል እንዳለሆነ የማስተማርና የመቀስቀስ፣ በሐሳብ የማሸነፈ ሃላፊነት ይኖርባቸዋል።
ስለዚህ መከባበሩ፣ እንደተጠበቀ፣ ቢቻል ሁለቱም ወደ አንድ አቋም እንዲመጡ ቢነጋገሩና በጋራ ቢሰሩ፣ ካልሆነም ግን የግድ አንዱ ሐሳብ አሸናፊ ሆኖ መውጣት ስላለበት የፖለቲካ ክርክሮቹ በሰለጠነ፣ ከስሜትና ከስድብ በጸዳ መልኩ ቢደረጉ ጥሩ ሊሆን ይችላል።
ከዚህ በፊት እንደጻፍኩት፣ ሰማያዊ የወሰደው ቅድመ ሁኔታ የማስቀመጣ ፖለቲካና አቋም ስህተተ ነው ብዬ ነው የማምነው። አንዳንዶች በምርጫው መሳተፉን «ተለጣፊ» እንደመሆን እና ለአገዛዙ ሌጂቲመሲ(እውቅና) እንደመስጠት አድርገው የሚቆጥሩ አሉ። እነዚህ ወገኖች አንድነት ወደ ምርጫ በመግባቱ «ተለጣፊ» ሆኗል የሚል አስተሳሰብ ካላቸው፣ መለስ ብለው የሚሊዮኖችን ንቅናቄ እንዲመለከቱ እጋብዛቸዋለው። በአሁኑ ጊዜ የሕዝብን ትርታ የያዘ፣ በሆያ ሆዬ ላይ ሳይሆን፣ በእውቀት ላይ የተመሰረተ ፖለቲካ የሚያራምድ ፣ በሁሉም ክልሎች መዋቅር ያለው የፖለቲካ ድርጅት አንድነት ብቻ ነው። ሂዱ አርባ ምንጭ፣ ሂዱ ጂንክ፣ ሂዱ ወሊሶ፣ ሂዱ ጊምቢ፣ ሂዲ ጎንደር፣ ሂዱ አሳሶ፣ ሂዱ አዳማ፣ ሂዲ ሶዶ፣ ሂዱ ደሴ …አንድነትን በዚያ ታገኛላችሁ።
ለአገዛዙ ሌጂቲመሲ መስጠት ነው ለሚሉት ደግሞ ሌጂቲመሲ ሰጭው ማን እንደሆነ ቢነገሩን ጥሩ ነበር። በዉጭ ኃይሎች ዘንድ ሕወሃት/ኢሕአዴግ ሌጂቲሚስ ያገኛል የሚል ፍርሃት ከሆነ ያላቸው፣ በጣም የዲፕሎማሲ እወቀት ዴፊሸንሲ አለባቸው ማለት ነው። እነአሜሪካ፣ ሕወሃት/ኢሕአዴጎች አምባገነን፣ በሕዝብ ያልተመረጡ፣ ድምጽ ሰርቀው ስልጣን ላይ ጠመንጃ ስለያዙ ብቻ፣ እየገደሉና እያሰሩ እንደሚገዙ ያውቃሉ። ሆኖም እውቅና ሰጥተዋቸው ዋይት ሃዉስ ድረስ ጠርተው እያስተናገዷቸው ነው። ለምን ሌላ፣ የተሻለ፣ ጥቅማቸውን የሚያስጤብቅ ኃይል ስለሌለ። እቅጩን እንወቅ፣ ቦይኮት ተደረገም አልተደረገም፣ ምርጫ ተገባም አልተገባም፣ አሜሪካም ሆነ አዉሮፓዉያን በአገዛዙ ላይ ያላቸውን አቋም አይለዉጥም። እነ አሜሪካ የፖሊሲ ለዉጥ የሚያደርጉት፣ ፊታቸውን ከሕወሃት/ኢሕአዴግ የሚያዞሩት፣ ተቃዋሚዎች ምርጫዉን ቦይኮት በማድረጋቸው ሳይሆን፣ ሕዝቡን አደራጅተው በሚሊዮኖች የሚቆጠሩትን ማነቃነቅ ከጀመሩ ብቻ ነው። ለዚህም ነው ምርጫ ከተገባ ሕወሃት/ኢሕአዴግ ሌጂቲማሲ እንዲያገኝ እናደርገዋለን የሚለው አስተያየት ዉህ የማይቋጥርና በእወቅት ላይ ያልተመሰረተ ነው የምለው።
ለጊዜው አበቃሁ !