የተከሰሱት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እስር ተፈረደባቸው

መንግሥት በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ሁከት ፈጥረዋል ተብሎ ክስ የተመሠረተባቸው የሰማያዊ ፓርቲ አባላት፣ በሁለት ወራት እስራት እንዲቀጡ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቂርቆስ ምብድ ችሎት ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ሰጠ፡፡

በሊቢያ አይኤስ የተባለው ቡድን በኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን አሰቃቂ ግድያ ለማውገዝ፣ መንግሥት ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በመስቀል አደባባይ በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ረብሻ በመፍጠር፣ በመሳደብና ድንጋይ በመወርወር ሰላማዊ ሠልፉን አውከዋል ተብለው የተከሰሱት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤተልሔም አካለወርቅ መሆናቸው ይታወሳል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ ሊከላከሉ እንዳልቻሉ ገልጾ ጥፋተኛ ካላቸው በኋላ፣ የቅጣት አስተያየት ጠይቋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ቅጣቱ ከብዶ እንዲቀጡ አመልክቷል፡፡ ተከሳሾቹም የቤተሰብ አስተዳዳሪ መሆናቸውን፣ በተለይ ወይንሸት ሞላ ረብሻ ተፈጠረ በተባለበት ዕለት ጠዋት የታሰረች መሆኗንና የታሰረችበትን ፖሊስ ጣቢያ ገልጻ ቅጣቱ እንዲቀልላት ጠይቃለች፡፡

ፍርድ ቤት በሰጠው ፍርድ ቅጣቱ ከብዶ እንዲቀጡ የሚለው የዓቃቤ ሕግን የቅጣት ማክበጃ አስተያየት የተቀበለ ቢሆንም፣ በቡድን ስለመረበሻቸው ያቀረበው ማስረጃ እንደሌለ ገልጿል፡፡ በመሆኑም እያንዳንዳቸው እጃቸው ከተያዘበት ጀምሮ ያለው ጊዜ ተቆጥሮ፣ በሁለት ወራት እስራት እንዲቀጡ ፍርድ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾቹ ሁለት ወራት ከአንድ ቀን የታሰሩ በመሆናቸው በዕለቱ እንዲፈቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ፍርደኞቹ የማስፈቻ ትዕዛዝ ተዘጋጅቶላቸው ከማረሚያ ቤት የተፈቱት ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ቢሆንም፣ ከማረሚያ ቤት ሲወጡ ተይዘው በፀጥታ ኃይሎች ወደ ፖሊስ ጣቢያ መወሰዳቸውን ሰማያዊ ፓርቲ አስታውቋል፡፡ 

 

 

መድረክ የሟች አባላቱ ቁጥር አራት መድረሱን አስታወቀ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ግንቦት 16 ቀን 2007 ከተካሄደው አምስተኛውን ዙር ጠቅላላ ምርጫ በኋላ፣ ለሞት የተዳረጉ አባላቱ ቁጥር አራት መድረሱን አስታወቀ፡፡

በዚህም መሠረት ቀደም ሲል መሞታቸው ከተነገረው ሦስት የመድረክ አባላት በተጨማሪ፣ በደቡብ ክልል በሐድያ ዞን ሶሮ ወረዳ በዳና ቶራ ቀበሌ ነዋሪና የመድረክ አባል ድርጅት የሆነው የኢትዮጵያ ማኅበረ ዴሞክራሲ ደቡብ ሕዝቦች አንድነት ፓርቲ (ኢማዴ-ደሕአፓ) መሠረታዊ ኮሚቴ አባል የነበሩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ መገደላቸውን አስታውቋል፡፡ 

‹‹በ2007 ጠቅላላ ምርጫ በቅስቀሳ ላይ ተሰማርተው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ የቆዩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ፣ ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ በመኖሪያ መንደራቸው በተፈጸመባቸው ድብደባ ከተገደሉ በኋላ ወንዝ ውስጥ ተጥለው ተገኝተዋል፤›› ሲሉ የመድረክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንደሻው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በሥፍራው ካሉ የፓርቲው አደረጃጀቶች መረጃ እንደሚሰባሰብ የገለጹት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹መጀመርያ ቀን ላይ በአካባቢው ያሉ ፖሊሶችንና ሌሎች ካድሬዎችን ያካተተ አካል እየተንቀሳቀሱ፣ ሟችንና ሌሎች ለመድረክ የምርጫ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አባላትና ወጣቶችን ‹የማዳበሪያ ሒሳብ እንዳይከፈል ሕዝቡም በመንግሥት ላይ እንዲያምጽ ቅስቀሳ እያደረጋችሁ ነው፤› በማለት ሟችንና ወጣቶችን ለማስፈራራትና ለማሰር ሲንቀሳቀሱ ነበር፤›› በማለት፣ አጋጠመ ያሉትን አስረድተዋል፡፡

‹‹በተለይ ‹ማዳበሪያን በሚመለከት ዕዳው እንዳይከፈል ያደረጋችሁት እናንተ ናችሁ› ተብለው ፖሊስ ሊይዛቸው ሲል ሸሽተው ነበር፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ሟች ሸሽቶ ከቆየበት ሥፍራ ምሽት ላይ ወደ ቤቱ በሚያመራበት ወቅት ነው ግድያው የተፈጸመበት፤›› በማለት የፓርቲውን አባል የአሟሟት ሁኔታ አስረድተዋል፡፡

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ በሥፍራው የመድረክ ተወካይና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ግለሰብ ስለሁኔታው ለማጣራት ፖሊስ ጣቢያ ቢሄዱም፣ በፖሊስ ጣቢያው የዕለት ሁኔታ መመዝገቢያ ላይ የተመዘገበው ‹‹ሰክሮ ውኃ ውስጥ ወድቆ›› የሚል እንደሆነ መመልከታቸውን፣ አቶ ጥላሁን ከደረሳቸው ሪፖርት ለመረዳት መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹የምናካሂደው ሰላማዊ ትግል ብዙ መስዋዕነት እንደሚያስከፍለን እናውቃለን፤›› ያሉት አቶ ጥላሁን፣ ‹‹ቢሆንም ግን ሰላማዊውን ትግል አጠናክረን እንቀጥላለን፤›› በማለት አስተያየታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ሟች አቶ ብርሃኑ ኤረቦ የ40 ዓመት ጎልማሳና የአምስት ልጆች አባት እንደሆኑ መድረክ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ ላይ አስታውቋል፡፡

መድረክ ከምርጫው ዕለት ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ አቶ ጊዲሳ ጨመዳ፣ በምዕራብ  አርሲ ዞን ቆራ ወረዳ አቶ ገቢ ጥቤ፣ እንዲሁም በትግራይ ክልል ምዕራብ ትግራይ ዞን በማይካድራ ከተማ አቶ ታደሰ አብርሃ የተባሉ ዕጩዎቹ መገደላቸውን ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

 

ማዕድን ሚኒስቴር በአገሪቱ የሕግ አግባብ መሠረት ባለመሥራቱ፣ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ የማዕድን ማምረት ሥራ ላይ ከተሰማራው ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ማግኘት የሚገባውን ከ429 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማሳጣቱን የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታወቀ፡፡

የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በማዕድን ሚኒስቴር ላይ በ2006 ዓ.ም. አጠቃላይ የሥራ አፈጻጸም ላይ ባደረገው የክዋኔ ኦዲት ነው መንግሥት ከፍተኛ ገንዘብ ማጣቱን ያረጋገጠው፡፡ 

የማዕድን ሥራ አዋጅን በተመለከተ የወጣው የ1986 ዓ.ም. አዋጅ ከከበሩ ማዕድናት ሽያጭ አምስት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ እንደሚወስን፣ ባልከበሩ ማዕድናት ላይ ምንም የሚለው ነገር እንደሌለ የኦዲተሩ የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ያስረዳል፡፡

ይህ አዋጅ ግን በአዋጅ ቁጥር 678/2002 መሻሻሉን በዚህ መሠረትም የከበሩ ማዕድናት ላይ ስምንት በመቶ የሮያሊቲ ክፍያ መጣሉን፣ ያልከበሩ ማዕድናት ላይ ስድስት በመቶ መጣሉን ሪፖርቱ ያትታል፡፡

ይሁን እንጂ ማዕድን ሚኒስቴር ከሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኩባንያ የከበሩና በከፊል የከበሩ ማዕድናት ላይ አምስት በመቶ ብቻ ሮያሊቲ ክፍያ በመሰብሰቡ፣ ከ2004 ዓ.ም.  እስከ 2006 በጀት ዓመት ከሚድሮክ የወርቅ ሽያጭ መንግሥት ሊያገኝ የሚችለውን 252.9 ሚሊዮን ብር ማጣቱን፣ እንዲሁም ካልከበሩ ማዕድናት በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ብቻ 413,394 ብር ማጣቱን፣ በድምሩ በሁለት ዓመታት ውስጥ 253.37 ሚሊዮን ብር ለመንግሥት ገቢ መደረግ የነበረበት የሮያሊቲ ገንዘብ አለመሰብሰቡን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር በ2000 ዓ.ም. ማምረት የጀመረ ቢሆንም፣ ማዕድን ሚኒስቴር ግን ይህንን ተቋም በየወቅቱ እየተከታተለ ሒሳባቸውን እንዳልመረመረ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማረጋገጡን ይገልጻል፡፡ ይህም በመሆኑ በሮያሊቲ ሥሌቶች ላይ በሕግ ማሻሻያዎች የሚመጡ ለውጦችን በመከተል የመንግሥትን ገቢ ለማስገባት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እንዳልቻለ ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪም መንግሥት በሚድሮክ የወርቅ ማዕድን አክሲዮን ማኅበር ላይ ያለውን የነፃ ድርሻ በሕግ አግባብ ማስላት ባለመቻሉ፣ እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ 108.7 ሚሊዮን ብር እንዲሁም እስከ መጋቢት 2006 ዓ.ም. ድረስ 67.4 ሚሊዮን ብር በድምሩ 176.2 ሚሊዮን ብር አገሪቱ ማጣቷን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡

ይህ በመሆኑም የተፈጠረውን ስህተት በማረም መንግሥት ያጣው ገንዘብ እንዲመለስ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማዕድን ሚኒስቴሩን አሳስቧል፡፡

 

ከ17.7 ሚሊዮን ብር በላይ መመዝበሩ ተጠቅሷል

በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የደቡብ ሱዳን ሊሚትድ ጁባ ቅርንጫፍ ከ17.7 ሚሊዮን ብር በላይ በተጭበረበረ መንገድ ለግለሰቦች እንዲውል አድርገዋል ተብለው የሙስና ክስ የተመሠረተባቸው አምስት የባንኩ ሠራተኞች፣ ዋስትና

ተከልክለው ወደ ማረሚያ ቤት ወረዱ፡፡ አንዲት የቅርንጫፍ ባንኩ ከፍተኛ ኦዲተር በዋስ ተለቀቁ፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ክስ የመሠረተባቸው የባንኩ ሠራተኞች፣ የሒሳብ ሹም አቶ ረሚላ ለወይ ኡስማን፣ የደንበኞች ሥራ አስኪያጅ አቶ ፍፁም ብርሃን ዓለም ስምኦን፣ ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ሀብታሙ ዮሴፍ ማርዬ፣ ማኔጂንግ ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ሚካኤል ተክለ እግዚ ገብረ ማርያም፣ የንግድ አገልግሎት መኰንን አቶ ደስታው ፈንታሁን መንበር (ያልተያዙ)፣ ዋና ኦዲተር ወ/ሮ ሙሉሸዋ ክብረት፣ እንዲሁም አቶ መሐመድ ሁሴን ጣቢር (ያልተያዙ) እና አቶ ሁሴን ለወይ ኡስማን የተባሉ ግለሰቦች ናቸው፡፡ 

የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ ሲቴፕ ፎር ትሬድ ኤንድ ኢንቨስትመንት ካምፓኒ ሊሚትድ የተባለ ድርጅት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጁባ ቅርንጫፍ ደንበኛ ነው፡፡ በባንኩ በኩል 4,360,000 ዶላር ኤልሲ በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ባንክ ይፈቀድለታል፡፡ ዶላሩ የሚለቀቅለት በሦስት ጊዜ ክፍያዎች ነው፡፡ ክፍያው የሚፈጸመው ገንዘቡ ኬንያ ወደሚገኘው ስታንቢክ ባንክ ከተላለፈ በኋላ ነው፡፡ የመጀመርያው 1,453,33 ዶላር ተልኮለታል፡፡ ለድርጅቱ የሚላከው ዶላር ከደቡብ ሱዳን ፓውንድ ጋር ተመጣጣኝ የሆነና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ባንክ ካለው ሒሳብ ተቀንሶ መሆኑን ክሱ ያስረዳል፡፡

ነገር ግን አንደኛ ተከሳሽ አቶ ረሚላ ለድርጅቱ የተላከውን የገንዘብ መጠን መቀነስ ሲገባው ሳይቀንስ መቅረቱን ክሱ ያክላል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ ሒሳብ ሲሠራ (Reconciliation) ሳይቀነስ የቀረው ገንዘብ ተንጠልጣይ ሆኖ ሲያየው ማዕከላዊ ባንኩ እንዲቀንስ ማድረግ ቢገባውም አለማድረጉ ክሱ ጠቅሷል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ በሌሉበት ክሱ በተመሠረተባቸው አቶ መሐመድ ሁሴን ጣቢር ስም በ200 የደቡብ ሱዳን ፓውድ አካውንት እንዲከፍቱ ማድረጋቸውም ተጠቅሷል፡፡ በመቀጠልም በተለያዩ ጊዜያት በድምሩ 3,008,813 የደቡብ ሱዳን ፖውንድ የያዙ አራት ቼኮች ወደ  ኬንያ ንግድ ባንክ ለቼክ ማጣራት በማዕከላዊ ባንኩ በኩል ሲላኩ፣ የኬንያ ባንክ በግለሰቡ ገንዘብ እንደሌለው የገለጸ ቢሆንም አንደኛው ተከሳሽ ቼኮቹንና ተያያዥ ቅጾችን በማጥናት ግለሰቡ ገንዘብ ያለው ማስመሰሉ ክሱ ያብራራል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ የዴቢት ትኬት በማዘጋጀትና ከሁለተኛ ተከሳሽ ጋር አቶ ፍፁም ብርሃን ጋር በጣምራ ፈርመው የተንጠለጠለው ገንዘብ መሐመድ ሁሴን በተባለ ተከሳሽ ስም ወደ ተከፈተው ሒሳብ እንዲገባ በማድረግ በባንኩ ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ በአጠቃላይ ገንዘቡ በኢትዮጵያ ብር ሲሰላ 17,768,589 ብር መሆኑን፣ ተከሳሾቹ በሥልጣን ያላግባብ መጠቀም የሙስና ወንጀል ክስ እንደተመሠረተባቸው የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

ተጠርጣሪ ተከሳሾቹ ከላይ የተገለጸውን ገንዘብ በሕገወጥ መንገድ የተገኘ መሆኑን እያወቁ፣ በሐሰተኛ መንገድ በስድስተኛ ተከሳሽ አቶ መሐመድ ስም በተከፈተ ሒሳብ የተቀመጠውን ገንዘብ ከተለያዩ አካውንቶች የተላኩ በማስመሰልና ወደተለያዩ የባንክ ሒሳቦች አዘዋውረናል፡፡ የተለያዩ ተሽከርካሪዎችን፣ አንድ ባለሁለት መኝታ የኮንዶሚኒየም ቤት በመግዛት፣ በአጠቃላይ አንደኛ ተከሳሽና ስድስተኛ ተከሳሽ የአንደኛ ተከሳሽን ወንድም ሰባተኛ ተከሳሽ አቶ ሁሴን ለወይንን በመጠቀም፣ ገንዘቡን ማቀናነሳቸውንና በሕገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስለው በማቅረብ የሙስና ወንጀል መከሰሳቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሹ አቶ ፍፁም ብርሃን ዓለም የወንጀል ሕግ አንቀጽ 411 (2)ን በመተላለፍ የመንግሥትን ሥራ በማያመች አኳኋን በመምራት በሕጋዊ መንገድ ማግኘት ከሚገባቸው በላይ 6,620,600 ብር ይዘው መገኘታቸውንና ይኼም የሙስና ወንጀል መሆኑን ክሱ ይገልጻል፡፡ ሦስተኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ ዮሴፍም ማግኘት ከሚገባቸው በላይ 8,298,880 ብር ከሕጋዊ ገቢያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸውን፣ አራተኛም ተከሳሽ አቶ ሚካኤል ተክለ እግዚም 27,930,429 ብር ከሕጋዊ ገቢያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸው፣ አቶ ደስታው ፋንታሁንም 2,684,876 ብር ከሕጋዊ ገበያቸው በላይ ይዘው በመገኘታቸው፣ በፈጸሙት ምንጩ ያልታወቀ ንብረትና ገንዘብ ይዞ መገኘት የሙስና ወንጀል መከሰሳቸውን ክሱ ያብራራል፡፡

በቅርንጫፉ ዋና ኦዲተር የነበሩት ወ/ሮ ሙሉሸዋ ክብረት ሒሳቦችን በአግባቡ ባለመቆጣጠራቸውና የሥራ ኃላፊነትን ባለመወጣት የሚፈጸም የወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸዋል፡፡ ተጠርጣሪ ተከሳሾቹ ችሎት ቀርበው ክሱ ከተነበበላቸው በኋላ በጠበቆቻቸው አማካይነት ክሱ ዋስትና እንደማያስከለክል፣ ምክንያቱ ደግሞ አዲስ በወጣው የኮሚሽኑ አዋጅ መሠረት ዋስትና የሚከለክል አንቀጽ መሻሩን ጠቅሰው በዋስ እንዲለቀቁ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ የተጠቀሰው አንቀጽ ዋስትና እንደሚከለክልና በአዲሱ አዋጅ ዋስትናን የሚመለከተው አንቀጽ እንዳልተሰረዘ በመግለጽ ጥያቄውን ተቃውሟል፡፡ ፍርድ ቤቱ የደቂቃዎች ረፍት ወስዶ በሁለቱ ወገኖች ክርክር ላይ ከተወያየ በኋላ፣ በድጋሚ በመሰየም ከኦዲተር በስተቀር ሌሎቹን ተከሳሾች ዋስትና ከልክሏቸዋል፡፡ ኦዲተሯም ዋስትና ተፈቅዶላቸዋል፡፡ የክስ መቃወሚያ ለመስማት ለሐምሌ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

 

 

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም በደረሱት የአስተዳደራዊ በደል ጥቆማዎች ላይ ተመሥርቶ በሚያደርገው ምርመራ የመፍትሔ ሐሳቦችን ቢያቀርብም፣ አንዳንድ መሥሪያ ቤቶች እምቢተኝነት እያሳዩ መሆናቸውን አስታወቀ፡፡ ከእነዚህም መካከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትልቁን ድርሻ እንደሚይዝ ገለጸ፡፡

 

ዋና የሕዝብ እንባ ጠባቂዋ ወ/ሮ ፎዚያ አሚን የተቋማቸውን የአሥር ወራት የሥራ ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት፣ በአስተዳደር ጥፋት ምክንያት የደረሰ በደል እንዲታረም የተመርማሪ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎች ትብብርና ድጋፍ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የአስተዳደር በደል አቤቱታዎች ሲደርሱት አልያም በተደጋጋሚ ከሚደርሰው ጥቆማ በመነሳት የራሱን ምርመራ እንደሚያደርግ የገለጹት ወ/ሮ ፎዚያ፣ በምርመራው መሠረት የመፍትሔ ሐሳቦችን ለሚመለከታቸው ተቋማት እንደሚልክና የመፍትሔ ተቀባይነትም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡

ሆኖም የተወሰኑ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች በተቋሙ የምርመራ ውጤት ላይ ተንተርሶ በተላከላቸው የመፍትሔ ሐሳቦች መሠረት አለመፈጸም ወይም የማይፈጸሙበት በቂ ምክንያት ካላቸው ለተቋሙ ያለመግለጽና በምርመራ ሒደት አስፈላጊውን ትብብር ያለማሳየት እንቢተኝነት እንደሚታይ ገልጸዋል፡፡

ከእነዚህም ተቋማት መካከል በተደጋጋሚ ስሙ የተገለጸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው፡፡ ከአስተዳደሩ አካላት መካከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና ክፍለ ከተሞች ይገኙበታል፡፡

በተጨማሪም የኦሮሚያ የአርሲ ዞን አስተዳዳር ጽሕፈት ቤት፣ የምሥራቅ ሸዋ ዞን አስተዳዳር ጽሕፈት ቤት፣ የሐዋሳ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና በሐረሪ ክልል የፍትሕና የፀጥታ ጉዳይ ቢሮ በእነዚህ ችግሮች የተጠቁ መሆናቸውን ዋና እንባ ጠባቂዋ ወ/ሮ ፎዚያ ገልጸዋል፡፡

የተገለጹት ተቋማት በቀረበላቸው የመፍትሔ ሐሳቦች መሠረት የእርምት ዕርምጃ ባለመውሰዳቸው ልዩ ሪፖርት ለፓርላማው የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳዳር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በዝርዝር መላካቸውን የጠቀሱት ወ/ሮ ፎዚያ፣  ቋሚ ኮሚቴው ባደረገው ክትትል በደሎቹ በከፊል የታረሙ መሆኑን ነገር ግን ሙሉ በሙሉ አለመቀረፋቸውን ገልጸዋል፡፡

ራሱ ተቋሙ ወደ ፍርድ ቤት በመውሰድ ለምን እነዚህን ተቋማት እንደማያስቀጣ የተጠየቁት ዋና እንባ ጠባቂዋ፣ በአስተዳደራዊ በደል አቤቱታ ላይ ምርመራን መሠረት ያደረገ የመፍትሔ ሐሳብ አቤቱታ ለቀረበበት ተቋም የሚቀርብ መሆኑን ገልጸው፣ ተቋሙ በቂ ምክንያት ካለው ይኼንኑ ገልጾ የመፍትሔ ሐሳቡን ላለመተግር እንደሚችል በአዋጁ መደንገጉን ተናግረዋል፡፡

‹‹በቂ ምክንያት ካለው›› የሚለው ሐረግ ለትርጉም ክፍት በመሆኑ ዕርምጃ ለመውሰድ እንዳላስቻላቸው የገለጹት ወ/ሮ ፎዚያ፣ ይኼን ችግር ለመቅረፍ አዋጁን ለማሻሻል በዝግጅት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) መንግሥት ድጎማ  እንዲያደርግለት ያዘጋጀውን ፕሮፖዛል፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ሊያቀርብ ነው፡፡

ታኅሳስ 26 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትሩና በኢሠማኮ አመራሮች መካከል በተደረገ የምክክር መድረክ ላይ፣ ኢሠማኮ ለመንግሥት ይደረግልኝ ብሎ ያቀረበውን ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቃል አወንታዊ ምላሽ ሰጥተው እንደነበር ይታወሳል፡፡

 

በዚሁ ምላሽ መሠረት ኢሠማኮ የመንግሥትን ድጎማ እሻባቸዋለሁ ያላቸውን ጉዳዮች በዝርዝርና በፕሮፖዛል መልክ አዘጋጅቷል፡፡ ያስፈልገኛል ያለውንም የገንዘብ መጠን በመጥቀስ  ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር አቅርቦ ነበር፡፡

ይህንን ፕሮፖዛል ያቀረበው ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ቢሆንም፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ምንም ዓይነት ምላሽ ሳይሰጠው ቆይቶ ነበር፡፡ ቆይቶም ግን ኢሠማኮ ለሚኒስቴሩ ያቀረበው ጥያቄ መቅረብ ያለበት ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ነው የሚል ምላሽ ስለተሰጠው፣ ‹‹ድጎማ ይሰጠኝ›› የሚለውን ጥያቄውን በድጋሚ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ለማቅረብ እየተዘጋጀ መሆኑን፣ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

‹‹መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግልን የፈለግነው ለግንዛቤ ማስጨበጫና ለአቅም ግንባታ ፕሮግራሞች ማስፈጸሚያ የሚውል ነው፤›› ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ይህንንም በፕሮፖዛላቸው ላይ ማስፈራቸውን ተናግረዋል፡፡

በተከታታይ በየዓመቱ የአሠሪና ሠራተኞችን ግንኙነት በሚመለከት የኢንዱስትሪ ሰላምን ለመፍጠር በሚያስችሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ ሁሉም ወገን መብትና ግዴታውን እንዲወጣ ለማድረግ ለሚያስፈልገው ወጪ መንግሥት ድጎማ እንዲያደርግ በኢሠማኮ ተጠይቋል፡፡ ሥልጠናዎቹና የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞቹ በአሠሪና በሠራተኛ ዘንድ አሉ የሚባሉትን ችግሮች ለመፍታት፣ ሠራተኛውና አሠሪውን የሚመለከቱ ሕጎች ምን እንደሚመስሉ ለማሳየትና በዚሁ መሠረት ተፈጻሚ እንዲሆን ለማስቻል ጭምር ነው፡፡ ድጎማው ለተፈለገው ዓላማ ብቻ የሚውል ነው ያሉት አቶ ካሳሁን፣ ከመንግሥት የሚገኘው የገንዘብ ድጎማ ለኢሠማኮ ውስጣዊ በጀት ወይም ለአስተዳደር ሥራ እንደማይውልና ደመወዝን ለመሰሉ ወጪዎች ማስፈጸሚያም እንደማይጠቀምበት ገልጸዋል፡፡

ኢሠማኮ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተመራው ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር አድርጎት በነበረው የምክክር መድረክ ላይ፣ ሊፈጸሙልኝ ይገባሉ ብሎ ካቀረባቸው ከ30 በላይ ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ ‹‹መንግሥት ኢሠማኮን ይደጉም›› የሚል ሲሆን፣ መንግሥትም ኢሠማኮን ለመደገፍ ፈቃደኝነቱን አሳይቷል፡፡

በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹ድጎማ የሚለው ቃል ጸያፍ ነው…በድጎማ ያደገ አገርና ድርጅት የለም፡፡ ሥራ ለመሥራት የገበያ ክፍተት ስላለ እንደ ልማታዊ መንግሥት ለዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አጋር ይሆናል ተብሎ እስከታመነ ድረስ በኢሠማኮ የተጠየቀውን እንሰጣለን፤›› ብለው፣ ‹‹ይህ ድጎማ ግን ለሽርሽር የምትጠቀሙበት አይደለም፤›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋቸው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ሠራተኞችን ማስጨብጨቡ ይታወሳል፡፡

በወቅቱ ሊፈቱልን ይገባል ተብለው ከኢሠማኮ ከቀረቡት ጥያቄዎች ውስጥ አብዛኞዎቹ አዎንታዊ ምላሽ እንዳገኙ የተነገረ ሲሆን፣ ከቀረጥ ነፃ ተሽከርካሪዎችም እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል፡፡ አሠሪዎች ለሠራተኞቻቸው የሚያቀርቡት ምግብ ታክስ እንዳይደረግ የሚለውም ጥያቄያቸው አወንታዊ ምላሽ እንዳገኘም ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

 

በአሁኑ ወቅት 85 በመቶ የተጠናቀቀው ከአዲስ አበባ-ጂቡቲ ድረስ እየተገነባ ያለው የባቡር መስመር በሚቀጥለው ዓመት አገልግሎት ይስጣል ተባለ፡፡

በሎስጂቲክስ ችግሮች ላይ መሠረታዊ ለውጥ ከማምጣቱም በላይ፣ ከውጭ ለሚገባ ከፍተኛ መጠን ያለው ማዳበሪያ ትራንስፖርት ተስፋ ተጥሎበታል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ግብዓት አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተወካይ አቶ በየነ ገብረ ሥላሴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ባቡሩ ሥራ የሚጀምር ከሆነ ማዳበሪያው ታሽጎ ወይም በብትን ይግባ የሚለው ይታያል፡፡ ነገር ግን ባቡሩ ሥራ ከጀመረ በብትን ማስገባቱ አዋጭ ይሆናል ሲሉ አቶ በየነ አስረድተዋል፡፡

ለሚቀጥለው ምርት ዘመን የሚፈለገውን ማዳበሪያ መጠን ለማወቅ ግብርና ሚኒስቴር ቅኝት እያደረገ መሆኑም ተገልጿል፡፡ ግብርና ሚኒስቴር ዘርፉ የሚፈለገውን የማዳበሪያ መጠንና ዓይነት ከክልሎች እየሰበሰበ ሲሆን፣ በይደር የሚቆየውን ማዳበሪያ መጠን በመገምገም ላይ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

የአገሪቱ ግብርና ዘርፍ የሚፈለገውን የማዳበሪያ መጠን እንደታወቀ፣ የግብርና ግብዓት አቅራቢ ኢንተርፕራይዝ በጥቅምት 2008 ዓ.ም. ጨረታ አውጥቶ ግዥ እንደሚፈጽም ተጠቁሟል፡፡

ለ2007 ዓ.ም. ምርት ዘመን 894 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ዩርያና ኤንፒኤስ ማዳበሪያዎች ግዥ ተፈጽሞ፣ አብዛኛው አገር ውስጥ መግባቱ ይታወሳል፡፡ አገር ውስጥ የገባው ማዳበሪያ በኩንታል 1,200 ብር አካባቢ በመሸጥ ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

ነገር ግን በ2007 ዓ.ም. ግዥ ከተፈጸመው ማዳበሪያ ውስጥ አንድ መርከብ ማዳበሪያ በአሁኑ ወቅት በጂቡቲ ወደብ በመራገፍ ላይ ይገኛል፡፡ አቶ በየነ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ግብርና ሚኒስቴር አገሪቱ የምትፈልገውን የማዳበሪያ መጠንና ዓይነት እንዳሳወቃቸው ግዥ ለመፈጸም ወደ ገበያ ይወጣሉ፡፡

የግብርና ሚኒስቴር ግብርና ግብዓት ዳይሬክተር አቶ ተሾመ ላቀው በበኩላቸው፣ ክልሎች የማዳበሪያ ፍላጎታቸውን በነሐሴ ወር እንደሚያሳውቁና በጥቅምት ወር ወደ ግዥ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

በዚህ የምርት ዘመን ግዥ የተፈጸመው 894 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ ሲሆን፣ አንዱ ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ ከ412 ዶላር እስከ 480 ዶላር ግዥ ተፈጽሟል፡፡ በምርት ዘመኑ ለማዳበሪያ ዘርፍ አስቸጋሪ ጉዳይ የነበረው የትራንስፖርት ጉዳይ ሲሆን፣ ይህም የሆነው ማዳበሪያን በዝቅተኛ ዋጋ ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ሲባል በትራንስፖርት ሒሳብ ላይ ተመን በመውጣቱ ነበር፡፡

ይህም የትራንስፖርት ድርጅቶችን ትኩረት መሳብ ባለመቻሉና በወቅቱ በርካታ ዕቃዎች ጂቡቲ ወደብ ደርሰው የነበረ በመሆኑ፣ ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ ለማጓጓዝ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡

አቶ በየነ እንዳሉት፣ በሚቀጥለው ዓመት ይህንን ችግር ለመፍታት ከወዲሁ ከባህር ትራንስፖርትና ከሎጂስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ጋር ንግግር ይጀመራል፡፡ ከአዲስ አበባ ጂቡቲ ድረስ በሚገነባው የባቡር መስመር ችግሩ ሊቀረፍ እንደሚችል አቶ በየነ ያላቸውን እምነት ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የዓለም አቀፍ የማዳበሪያ ዋጋም በዚህ የምርት ዘመን ከተገዛበት ዋጋ ቅናሽ ይኖረዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የሚናገሩት አቶ በየነ፣ በሚቀጥለው ምርት ዘመን ለአርሶ አደሩ የሚቀርበው ማዳበሪያ የዋጋ ቅናሽ ሊኖረው ይችላል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ዘርፍ የሚፈልገው ማዳበሪያ መጠን እያደገ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ አፈሩ የሚፈልገው ማዳበሪያ ዓይነትም ተለይቶ እንደታወቀ ተገልጿል፡፡ በግብርና ዘርፍ ውስጥ ብዙም  የማይታወቀው ኤንፒኤስ ማዳበሪያ፣ የአገሪቱን ግብርና የተቀላቀለ በመሆኑ በአገሪቱ አምስት ማዳበሪያ ፋብሪካዎችም አፈሩ የሚፈልገውን ማዳበሪያ በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

 

ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ምርጫውን ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን ምርጫ ቦርድ አረጋገጠ

‹‹መድረክና ሰማያዊ ፓርቲዎች ሁለተኛና ሦስተኛ ሆነዋል›› ፕሮፌሰር መርጋ በቃና

-የጊምቦ ገዋታ የምርጫ ውጤት አልተካተተም

በመላው ኢትዮጵያ (ከጊምቦ ገዋታ ምርጫ ጣቢያ በስተቀር) ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የተካሄደውን የሕዝብ ተወካዮችና የክልል ምክር ቤቶች አገራዊ ምርጫ ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን፣

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በሒልተን ሆቴል ይፋ አደረገ፡፡

የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና እንደገለጹት፣ ቦርዱ በአዋጅ ቁጥር 532/99 አንቀጽ 77 መሠረት አጠቃላይ የምርጫውን ውጤት ይፋ ያደርጋል፡፡ በመሆኑም ለአምስተኛው አገራዊ ምርጫ 36,851,461 ሕዝብ በመራጭነት ተመዝግቦ፣ 34,351,444 ሕዝብ ድምፁን ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ኢሕአዴግና አጋር ድርጅቶቹ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 334 ወንዶችና 212 ሴቶች በዕጩነት አቅርበው አሸናፊ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ምክር ቤቱ ካለው 547 መቀመጫዎች 546ቱን ሲያሸንፉ፣ ላለፉት አምስት ዓመታት ብቸኛው የግል የፓርላማ አባል የነበሩት ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስና የኢሕአዴግ ዕጩ ዶ/ር መብራቱ ገብረ ማርያም (የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት) የሚወዳደሩበት የቦንጋ ጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል ውጤት  ይፋ ባለመደረጉ፣ ከተገለጸው ውጤት ጋር አለመካተቱን ሰብሳቢው ተናግረዋል፡፡

ለክልል ምክር ቤቶች ኢሕአዴግና አጋሮቹ፣ 1187 ወንዶችና 800 ሴቶች በድምሩ 1,987 አባላት በዕጩነት አቅርበው ሙሉ በሙሉ ማሸነፋቸውን ፕሮፌሰሩ አክለዋል፡፡

ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 52 የፖለቲካና ዘጠኝ የግል ዕጩዎች ለ547 መቀመጫዎች የተወዳደሩ ቢሆንም፣ ኢሕአዴግ በአምስት ክልሎች ማለትም በአማራ፣ በትግራይ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በሐረሪ፣ በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች 27,347,332 ድምፅ በማግኘት 500 መቀመጫዎችን ያለምንም ተቀናቃኝ ማሸነፉን ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡

ለሁለቱ ምክር ቤቶች 40,536,607 የድምፅ መስጫ ወረቀቶች መቅረቡን የገለጹት ፕሮፌሰሩ፣ 1,130,390 ድምፅ መስጫ ወረቀቶች ዋጋ አልባ መሆናቸውንና 520,379 ድምፅ መስጫዎች መበላሸታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምርጫ ውድድሩ መድረክና ሰማያዊ ፓርቲዎች ሁለተኛና ሦስተኛ መውጣታቸውን የገለጹት ፕሮፌሰር መርጋ፣ የምክር ቤቶቹን መቀመጫዎች የሚያስገኝ ድምፅ ባለማግኘታቸው ተሸናፊ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡ ቦርዱ የሕዝብ ድምፅ ማስከበር እንዳለበት የተናገሩት ሰብሳቢው፣ ይኽንኑ ተግባራዊ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡ በደቡብ ክልል የጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል የምርጫ ውጤት ለቦርዱ መድረሱን ጠቁመው፣ ቦርዱ ውጤቱን ባለማፅደቁ በዕለቱ በገለጹት ውጤት ላይ አለመካተቱን፣ ነገር ግን  በቅርቡ ፀድቆ በቦርዱ ድረ ገጽ ይፋ እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡

ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. በደቡብ ክልል በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ በጊምቦ ገዋታ ምርጫ ክልል በተካሄደው ምርጫ፣ የኢሕአዴግ ዕጩ ዶ/ር መብራቱ ገብረ ማርያም የግል ዕጩውን ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስን በሰፊ ውጤት ማሸነፋቸውን ከምርጫ ጣቢያዎቹ ከተገኘው መረጃ መረጋገጡን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

 

የትራፊክ መጨናነቅን ለመቀነስ አዲስ አበባ እስከ አዳማ የተገነባው የፍጥነት መንገድ አካል የሆኑ ሁለት መንገዶች በከፊል ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ሊሆኑ ነው፡፡

ከአቃቂ ለቡና ከአቃቂ የረር በመገንባት ላይ ያሉት መንገዶች አንደኛው መስመራቸው ለትራፊክ ክፍት እንዲሆን፣ ግንባታቸው በፍጥነት እንዲካሄድ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡

ሁለቱ መንገዶች ግንባታቸው በየካቲት 2008 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ ቢታቀድም፣ በአካባቢው እየተፈጠረ ያለው የትራፊክ መጨናነቅ በጣም እየጨመረ በመምጣቱ ትራንስፖርት ሚኒስቴር በሰጠው መመርያ፣ አንደኛው ረድፍ በአፋጣኝ ተገንብቶ ለትራፊክ ክፍት እንዲሆን ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡

በዚህ መሠረት የቻይናው ግዙፍ የኮንስትራክሽን ኩባንያ ሲሲሲሲ ግንባታው በማገባዳደድ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት እንደሚደረግ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጠን ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ሳምሶን ወንድሙ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የፍጥነት መንገዱ መጨረሻ ከሆነው አቃቂ ተነስቶ ለቡ ድረስ ያለው 13.6 ኪሎ ሜትር እና ከአቃቂ ተነስቶ አይሲቲ ፓርክ (የረር ጎሮ) ድረስ የሚገነቡት መንገዶች ናቸው ለትራፊክ ክፍት የሚሆኑት፡፡

እነዚህ መንገዶች በአጠቃላይ ስድስት መኪኖችን በአንድ ጊዜ የሚያስተላልፉ ሲሆን፣ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት የሚሆነው አንደኛው ረድፍ ሦስት መኪኖችን በአንድ ጊዜ ያስተላልፋል ተብሏል፡፡ በአጠቃላይ ሁለቱ የመንገድ ፕሮጀክቶች 4.6 ቢሊዮን ብር ወጪ የሚደረግባቸው ሲሆኑ፣ ከአጠቃላይ ወጪ 75 በመቶ የቻይና ኤግዚም ባንክ ቀሪውን 25 በመቶ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ይሸፍናሉ፡፡

የመንገዶቹ ግንባታ ባለፈው 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ነው የተጀመረው፡፡ በሁለት ዓመት ከስምንት ወር ይጠናቀቃል ተብሏል፡፡ ነገር ግን አንዱ ረድፍ የግድ ማለቅ አለበት በመባሉ ግንባታው እየተፋጠነ በመሆኑ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት ይሆናል፡፡

እነዚህ ሁለት መንገዶች ከአዲስ አበባ-አዳማ ድረስ የተገነባው ግዙፍ የፍጥነት መንገድ አካል ናቸው፡፡ የአዲስ – አዳማ የፍጥነት መንገድ 84.6 ኪሎ ሜትር ርዝመት ሲኖረው  12.2 ቢሊዮን ብር ወጥቶበታል፡፡ ሁለቱ መንገዶች እንደተጠናቀቁ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ከቃሊቲ እስከ አቃቂ ድረስ ያለውን መንገድ ደረጃ የሚያሻሽል መሆኑ ታውቋል፡፡

ይኼ መንገድ ብቸኛው የአገሪቱ ወጪና ገቢ ንግድ የሚከናወንበት በመሆኑ ተለዋጭ መንገድ ሳይገነባ የመንገዱን ደረጃው ማሻሻል አይቻልም ተብሎ ቆይቷል፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት የፍጥነት መንገዱ በሁለት አቅጣጫዎች ወደ አዲስ አበባ ከተማ በመዘርጋቱ፣ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ወደ ግንባታ ይገባል በማለት ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ፍቃዱ ኃይሌ አገር ውስጥ ባለመኖራቸው አስተያየታቸውን ማካተት ሳይቻል ቀርቷል፡፡

 

ትውልደ ኢትዮጵያዊው ገጣሚና ጸሐፊ ተውኔት የማንቸስተር ዩኒቨርሲቲ ቻንስለር ሆነ

በእንግሊዝ ማንችስተር ዩኒቨርሲቲ ለቻንስለርነት ከተወዳደሩ ሦስት ግለሰቦች መካከል ትውልደ ኢትዮጵያዊው ገጣሚና ጸሐፈ ተውኔት ለምን ሲሳይ አብላጫውን ድምፅ በማግኘት አሸነፈ፡፡

ለምን በወድድሩ የተሳተፉትን የሙዚቃ ባለሙያውን ሰር ማርክ ኤልደርና የቀድሞውን የእንግሊዝ ፖለቲከኛ ሎርድ ፒተር ማንዴልሰንን ሰፊ በሆነ የድምፅ ብልጫ አሸንፏል፡፡

ለምን ውድድሩን ያሸነፈው 7,131 የማንቸስተር ዩኒቨርሲቲ ሠራተኞችና የቀድሞ ተማሪዎችን ድምፅ በማግኘት ሲሆን፣ ሰር ማርክ ኤልደር 5,483 ድምፅ በማስመዝገብ ሁለተኛ ሆነዋል፡፡ እንዲሁም ፖለቲከኛው ሎርድ ፒተር 5,269 ድምፅ በማግኘት ሦስተኛ ሆነዋል፡፡

ለምን ከምርጫው በኋላ የዩኒቨርሲቲው ቻንስለር ለመሆን ያበቃውን ድምፅ የሰጡትን መራጮች አመስግኗል፡፡ ከነሐሴ አንድ ጀምሮ በሥልጣን ላይ ያሉትን ቶም ብሎክሳምን ተክቶ ለሰባት ዓመታት እንደሚሠራ ታውቋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ዴም ናንሲም ዩኒቨርሲቲውን በማስተዋወቅ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡ 

ገጣሚና ጸሐፊ ተውኔት ለምን ሲሳይ እ.ኤ.አ. በ1967 በዊጋን ከተማ ከኢትዮጵያዊ ቤተሰቦች የተወደለ ሲሆን፣ ከወላጆቹ ዘንድ ለማደግ አልታደለም ነበር፡፡ እስከ 12 ዓመቱም እንግሊዛዊ አሳዳጊዎቹ ዘንድ ቆይቷል፡፡ በኋላም በአካባቢው በሚገኝ ሕፃናት ማሳደጊያ ዕድሜው 17 እስኪሆን ቆይቷል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1988 በ21 ዓመቱ የግጥም መድበል አሳትሟል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1995 ‹ኢንተርናል ፍላይት› የሚባል በቢቢሲ ዘጋቢ ፊልም አዘጋጅቶ ለዕይታ አብቅቷል፡፡ ሌሎች በርካታ ስኬቶችም ተቀዳጅቷል፡፡

 

ኢሳት ዜና (ሰኔ 17, 2007) የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሰኞ ከእስር እንዲፈቱ የወሰነላቸው አራት የፓርቲ አባላት ከእስር ቤት ከወጡ በኋላ የመንግስት ጸጥታ ሀይሎች በድጋሚ በቁጥጥር ስር ውለዋል። አራቱ ተከሳሾች ፍርድ ቤት ከተከሳሾች ፍርድ ቤት ካስተላለፋቸው ከሁለት ወር በላይ በእስር ቤት በመቆየታቸው ምክኒያት ሰኞ ከእስር እንዲፈቱ ውሳኔ መተላለፉ ይታወሳል። አራቱ ተከሳሾች ማክሰኞ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንዲወጡ …

ኢሳት ዜና (ሰኔ 17 2007) በቀጣዩ ወር በኢትዮጵያ ጉብኝት የሚያደርጉት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከተለያዩ አለም አቀፍ ተቋማት ተቃውሞ እንደገጠማቸው የእንግሊዙ ዘጋርዲያ ጋዜጣ የተለያዩ አካላትን ዋቢ በማድረግ ዛሬ ረቡእ ዘገበ። አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ፕሬዚዳንቱ በሰብአዊ መብት ረገጣና አፈና የምትታወቅ ሃገርን ለመጎብኘት መወሰናቸው ተገቢ እንዳልሆነ በመግለጽ ላይ መሆናቸውንም ጋዜጣው አስነብቧል። የፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ …

አለም ዝም ያለው, ታላላቅ ሀያላን ሀገራት ሁሉ ፀጥ ብለው ተመልካች የሁኑበት አረመኔያዊው እውነተኛው ትርኢት በጭራሽ አላባራም. እንዲያውም ብሶበታል. ሶሪያ ደበነች, ኢራቅን ፈጁት, ሊቢያ ን አናወዟት, ግብፆችን አረዱ, ኢትዮጵያዊንኑ ወንድሞቻችን ደገሙ. ኮሪያ, አሜሪካ, ኤርትራ ብቻ ያልነካኩት የለም ግን ዝም ተብለዋል. ሀይ ባይ አልተገኘም. አንድ ቡድን አለምን ሲያስጨነቅ አለም መሪዎች ያጣች ይመስላል. ነገሩ ግራ የገባ ነው. ልምምዳቸው […]

ሰኔ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ያሬድ ንጉሴ የተባለ ባለፈው ወር አውሮፓ የገባ አንድ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ለኢሳት እንደገለጸው በቅርቡ 25 ኢትዮጵያውያንና 2 ኤርትራውያን ሆነው ከሱዳን ወደ ሊቢያ ሲጓዙ፣ ደንጎላ በምትባል ቦታ ላይ በሱዳን የመከላከያ ሰራዊት አጃቢነት የመጣ ኢትዮጵያዊ የደህንነት ሰራተኛ የ48 አመት ጎልማሳ የሆነውን ኢትዮጵያዊ ግለሰብ ከመኪና አስወርዶ በሽጉጥ እንደገደለው ገልጿል። …

ሰኔ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ ባለፉት ጥቂት ወራት በተቃዋሚ መሪዎች ላይ የተፈጸመው ግድያና በመላ አገሪቱ በተቃዋሚ ድርጅት አባላት ላይ የሚፈጸመው የሰብአዊ መብት ረገጣ በቅርቡ በተካሄደው ምርጫ ላይ ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ነው ብሏል። የአፍሪካ ህብረትና የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የተፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን መርምረው ሪፖርት አለማድረጋቸውንም ድርጅቱ ወቅሷል። ምርጫው እስከሚካሄድበት ጊዜ …

ሰኔ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በእንግሊዝ አገር የሚገኘው ሪፕሪቭ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ የእንግሊዙ ጠ/ሚኒስቲር ዴቪድ ካሜሩን አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስዱ ጠይቋል። አቶ አንዳርጋቸው ለአንድ ሳምንት መታሰራቸው ረጅም መሆኑ ሳያንስ ለአንድ አመት ታስረው መቆየታቸው ለማሰብም የሚከብድ ነው ሲል የህግ ድጋፍ በመስጠት የሚታወቀው የሰብአዊ መብት ድርጅቱ ገልጿል። በእንግሊዝ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በሪፐሪቭ ዌብሳይት …

ሰኔ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአሁኑ ወቅት የአቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ አማካሪ የሆኑት ዶ/ር አርከበ ዕቁባይ ሰሞኑን ከመንግስት መገናኛ ብዙሃን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ዕቅዱ የተለጠጠ መሆኑን አምነው ሙሉ በሙሉ ላለመሳካቱ ምክንያት ያሉዋቸውን ምክንያቶች ዘርዝረዋል፡፡ የመጀመሪያው የእድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በባህርይው መዋቅራዊ ለውጥን ታሳቢ ያደርጋል፡፡ ይህ ዕቅድ በራሱ ተለጥጦአል ብለዋል፡፡ የፋይናንስ ምንጭ ማፈላለጉ …

ሰኔ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- መንግስት ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም አይሲስ በኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን ዘግናኝ ድርጊት ለመቃወም በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ድርጊቱን ለማውገዝ በስፍራው ተገኝታ የነበረችው ወ/ሮ ንግስት ወንዲፍራው ምክንያቱ ባልታወቀ ሰበብ ከ3 አመት ልጇ ጋር ግንቦት 19/2007 ዓ.ም ያለ ማዘዣ በፖሊስና በደኅንነት ኃይሎች ተወስዳ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ከታሰረች በሁዋላ ሰኔ …

ቪኦኤ በየዕለቱ ከምሽቱ 3 ሰዓት በኢትዮጵያ ኣቆጣጠር ጀምሮ በአማርኛ፣ በአጭር ሞገድ 22፣ 25 እና 31 ሜትር ባንድ የ60 ደቂቃ ሥርጭቱ ዜና፣ አበይት ዜናዎች ትንታኔና ሌሎችም ወቅታዊ መረጃዎችን የያዙ ፕሮግራሞች ያስተላልፋል።

ረቡዕ፡- ዴሞክራሲ በተግባር፣ ሴቶችና ቤተሰብ፣ አሜሪካና ሕዝቧ፣ ኢትዮጵያዊያን ባሜሪካ

ዮሃንስ ደሳለኝ (ጀርመን – ፍራንክፈርት)

Ethiopia Zare (ማክሰኞ ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም.  June 23, 2015)፡- በጀርመን ፍራንክፈርት ትላንት ሰኞ ሰኔ 15,2007 (June 22,2015) የእንግሊዝ ኮንስለር ፅ/ቤት የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ። በዚሁ ታጋይ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን በኩል ለኢትዮጵያ መንግሥት ተላልፈው የተሰጡበትን 1ኛ ዓመት ለማስታወስና እንዲሁም ላለፉት አንድ ዓመት ሁኔታዎችን በለዘብተኝነት የምትመለከተው ታላቋ ብሪታንያ ለራሷ ዜጋ ምንም ዓይነት ድጋፍና ከለላ ባለመስጠቷ ለማውገዝና አስፈላጊውን እርምጃ እንድትወሰድ ለማሳሰብ የተጠራው የተቃውሞ ሠልፍ ከጅምሩ ደማቅና አላማውን ያሳካ ነበረ።IMG_1874.JPG

ሙሉውን አስነብበኝ …

ቪኦኤ በየዕለቱ ከምሽቱ 3 ሰዓት በኢትዮጵያ ኣቆጣጠር ጀምሮ በአማርኛ፣ በአጭር ሞገድ 22፣ 25 እና 31 ሜትር ባንድ የ60 ደቂቃ ሥርጭቱ ዜና፣ አበይት ዜናዎች ትንታኔና ሌሎችም ወቅታዊ መረጃዎችን የያዙ ፕሮግራሞች ያስተላልፋል።

ማክሰኞ፡- ሐኪሙን ይጠይቁ፣ ንግድ፣ ምጣኔ ኃብትና ግብርና

አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ አሁንም ስቃይ ላይ መሆናቸው በኬንያ ወያነ የላካቸው ደህንነቶች ከተለያዩ የመገናኛ መሳሪያዎች ጋር በቁጥጥር ስር መዋላቸው የአቢሲኒያ ባንክ ሰራተኞች የተቃዋሚ ድርጅት ደጋፊ ናቸው ተብሎ በኢሕ አዴግ ባለስልጣናት መፈረጃቸው በሁመራ አሸባሪዎች ገቡ በሚል ሽፋን ህወሃት ህዝቡን እያሸበረ መሆኑን ተነገረ የሰማያዊ ፓርቲ የምስራቅ ጎጃም ዞን ፀኃፊ ሳሙኤል አወቀ በወያኔ ጭፍሮች ባሳለፍነው ሳምንት መገደሉ ተሰምታልFiled under: NEWS […]

መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስረው ሰኔ 15/2007 ዓ.ም በቄራ ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት እንዲፈቱ የተወሰነላቸው ወንይሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤትሄልየም አካለ ወርቅ ዛሬ ሰኔ 16/2007 ከእስር ተፈትተው ሲወጡ በፖሊስና ደህንነቶች ታፍነው ታስረዋል፡፡ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ታስረው የነበሩት ኤርሚያስ ፀጋዬና ዳንኤል ተስፋዬ ከእስር ከተፈቱ በኋላ የ6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ፖሊሶች […]

ሰኔ ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ምርጫ ቦርድ ጊዚያዊ ውጤቱን ይፋ ባደረገበት ወቅት የ105 ወንበሮችን ጉዳይ ግልጽ ባለማድረጉ አንዳንዶች “ኢህአዴግ ለተቃዋሚዎች ለመካፋፈል አስቦ ያደረገው ሊሆን ይችላል” በማለት አስተያየት ሲሰጡ ቢቆዩም፣ ቦርዱ ግን ኢህአዴግ መቶ በመቶ ምርጫውን አሸንፋል በማለት የመጨረሻ ውሳኔውን ሰጥቷል። ዋናዎቹ የተቃዋሚ ድርጅቶች ሰማያዊ ፓርቲና መድረክ ምርጫውን ” አሳፋሪ” ነው …

ሰኔ ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ችሎቱን የተከታተሉት በአቶ ማሙሸት የሚመራው መኢአድ ምክትል ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ለኢሳት እንደገለጹት አቶ ማሙሸት፣ ሰኔ 10፣ 2007 ዓም በ5 ሺ ብር ዋስ እንዲወጣ ፍርድ ቤት የወሰነ ቢሆንም፣ ፖሊስ ለመልቀቅ ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቶ ዛሬ ፍርድ ቤት አቅርቦታል። ፖሊስ፣ አቶ ማሙሸት ቢፈታ በምስክሮቼ ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ ሊያደርስባቸው …

ሰኔ ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከሰሞኑ በአዲስ አበባ የሚገኙ የታክሲ አገልግሎት ሰጪ የግል ባለንብረቶች ወደ አዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት ጽ/ቤቶች ታፔላ ለመቀየር በሄዱበት ወቅት ከተለመደው የታፔላ ማስቀየሪያ አገልግሎት ክፍያ ውጪ ባልተጠበቀ ሁኔታ የ1ሺ ብር ቦንድ ካልገዛችሁ የሚል ግዳጅ ተጥሎባቸዋል ። “አሁንስ ወዴት እንሂድ? ለማን አቤት እንበል?” በማለት የታክሲ ባለንብረቶች ሲያማርሩ …

ሰኔ ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አቶ አንዳርጋቸውን ጨምሮ ሌሎች በእስር ላይ ያሉ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ የሙስሊም የመፍትሄ አፈላላጊ የኮሚቴ አባላትና የሲቪክ ማህበረሰብ አባላት እንዲፈቱ የሚጠይቅ የተቃውሞ ሰልፍ በተለያዩ የአውሮፓ ከተሞች ከዛሬ ምሽት ጀምሮ ይካሄዳል። በጀርመን በፍራንክፈርት፣ሙኒክ፣ዱስልዶርፍ እና በርሊን የሚካሄድ ሲሆን፣ በፍራንክፈርት የሚደረገው ተቃውሞ ለ24 ሰአታት ይቆያል። በጣሊያን ሮማ፣ በቤልጂየም ብራሰልስ፣ በእንግሊዝ …

ቪኦኤ በየዕለቱ ከምሽቱ 3 ሰዓት በኢትዮጵያ ኣቆጣጠር ጀምሮ በአማርኛ፣ በአጭር ሞገድ 22፣ 25 እና 31 ሜትር ባንድ የ60 ደቂቃ ሥርጭቱ ዜና፣ አበይት ዜናዎች ትንታኔና ሌሎችም ወቅታዊ መረጃዎችን የያዙ ፕሮግራሞች ያስተላልፋል።

ሰኞ፡- ስፖርት፣ አፍሪካ ነክ ርዕሶች፣ ጤና

ዛሬ ቤተ እስራኤላዊያን ሰላማዊ ስልፍ  በቴል አቪብ ያደርጋሉ ምክንያቱም ባለፍው ቤተ እስራኤላዊ በፖሊስ ተመቶ ነበር ፖሊሱ እስር ቤት መግባት አለበት ብለው ሲጠይቁ የተሰጠው መልስ መጀመሪያ የተማታው ቤተ እስራኤላዊ ነው ፖሊሱ አይድለም የሚል ነበር ይህን ያስቆጣቸው ቤተ እስራኤላዊያን ዝም ብለው አልተመለከቱም በዛሬው እለት በአደባባይ ይወጣሉ አንድ ፍክራ አላቸው ይህም አንድ ሰው ለሁሉም ነው ሁሉም ለአንድ ሰው […]

የኢትዮጵያ መንግስት ያሰማራቸው ሰላዮች በህዝብ ጥቆማ ቢያዙም መለቀቃቸው ህዝቡን አስቆጥቷል ትናንት ረፋድ አካባቢ በናይሮቢ ነዋሪ የሆኑ ሶስት የፖለቲካ ስደተኛ ኢትዮጵያዊያን በኬንያ ፖሊስ ለጥያቄ እንደሚፈለጉ ተነግሯቸው ሲወሰዱ በዛ ያሉ ሰዎች ተፈላጊዎቹን በመከተል ፖሊስ ጣብያ ድረስ በማምራት የተያዙት እንዲለቀቁ አልያም ተላልፈው ለኢትዮጰያ መንግስት እንዳይሰጡ በመጠየቅ ምላሽ ካላገኙ ፖሊስ ጣብያውን እንደማይለቁ በማስረዳታቸው የፖሊስ ጣብያው ኃላፊዎች ሰዎቹን አሳልፈው እንደማይሰጡ […]

በኦሮሚያ ክልል፤ ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ድምፃችን ተሰረቀ በማለት ወደ ዩኒቨርሲቲ አስተዳዳሪዎች አቤቱታቸው ስላቀረቡ ብቻ በስርዓቱ ታጣቂዎች ጥይት እንደተተኮሰባቸው ተገለፀ። በምንጮቻችን መረጃ መሰረት በመቱ ዩኒቨርሲቲ የተካሄደውን ምርጫ አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ለተቃዋሚ ድርጅቶች መምረጣቸውን የተረዱት የስርዓቱ ካድሬዎች የምርጫው ኮረጆ ሰርቀው በመቀየር ኢህአዴግ 1568 አብላጫ በማግኘት አሸንፈዋል በማለት ግንቦት 17/ 2007 ዓ/ም ይፋ ያደረጉትን ውጤት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ስላልተቀበሉት ዓመፅ […]

«ትናንት፣ ዛሬም ሆነ ነገ የትግራይ ሕዝብ ጠላት ዐማራው ስለሆነ፣» እያንዳንዱ ትግሬ ዐማራን በማጥፋት እንቅስቃሴ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆን፣ የወያኔ የአገር-ውስጥ እና የውጭ የስለላ ቡድኖች ከፍተኛ አመራሮች በጥናቶቻቸው እንዳሣዩ የታመኑ የሞረሽ-ወገኔ ምንጮቻችን አረጋገጡ። የመረጃ ምንጮቻችን እንደሚያስረዱት፣ አጥኚዎቹ ከሕወሓት ፖሊት ቢሮ በተሰጣቸው መመሪያ መሠረት የትግሬ-ወያኔን ዘረኛ አገዛዝ ያለፉትን የ፳፬(ሃያ አራት) ዓመታት ጉዞ መዝነው፣ ለሥልጣኑ አስጊው ማን እንደሆነ በመተንተን፣ […]

The post የትግሬ-ወያኔ አመራር በቅርቡ ባደረገው ስብሰባ ዐማራን ፈጽሞ ሳያጠፋ እንቅልፍ እንደማይወስደው ዳግም አረጋገጠ! appeared first on ሳተናው .

ቪኦኤ በየዕለቱ ከምሽቱ 3 ሰዓት በኢትዮጵያ ኣቆጣጠር ጀምሮ በአማርኛ፣ በአጭር ሞገድ 22፣ 25 እና 31 ሜትር ባንድ የ60 ደቂቃ ሥርጭቱ ዜና፣ አበይት ዜናዎች ትንታኔና ሌሎችም ወቅታዊ መረጃዎችን የያዙ ፕሮግራሞች ያስተላልፋል።

ዕሁድ፡- ራዲዮ መፅሔት፣ መስተዋት (የወጣቶች ፕሮግራም) – ሁለቱ ዝግጅቶች በየሣምንቱ ይፈራረቃሉ፡፡

በጭካኔ ጥበብ ተንኮል የተካኑ፤ ስብዕናን ያጡ ለውነት የመከኑ፤ በሐሰት ተጠምቀው በውሸት የፀደቁ፤ በሌላው መከራ ሳቁ ተሳለቁ:: ሊጥሉት ሞክረው አልወድቅም ቢላቸው፤ ቀጥቅጠው ገደሉት በፈሪ ዱላቸው። በድቅድቅ ጨለማ ተስፋ በታጣበት፤ የነፃነት ትግል በደበዘዘበት፤ ሣሙኤል አወቀ እንደሻማ በርቷል፤ ለወገኑ ክብር በሕይወቱ ከፍሏል። ፈለጉን ተከተል አደራ ብሎሃል፤ ደሙ ከአጥናፍ አጥናፍ ይጣራል ይጮሃል፤ እምቢ በል ወገኔ ተነሣ ይልሃል፤ ፀጥ ያለው […]

ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሠራተኞች መልቀቅ ችግር ሆኖብኛል አለ

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በክፍያና በሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ማነስ ምክንያት፣ በጣም በርካታ ሙያተኞች መልቀቃቸውንና በምትካቸውም ብቁ ሙያተኛ ለመቅጠር ክፍያው ሳቢ አለመሆኑን ገለጸ፡፡ 

የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ጥሩነህ ዜና ያለፉትን አሥራ አንድ ወራት የኮሚሽኑን የዕቅድ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት ነው ይኼንን ችግር ያነሱት፡፡

እንደ ኮሚሽነሩ ገለጻ፣ 12 ወንዶችና ሰባት ሴቶች በድምሩ 19 ሠራተኞች ሥራቸውን ለቀዋል፡፡ መሥሪያ ቤቱ ሠራተኞች መልቀቅና በምትካቸው መቅጠር ባለመቻሉ ባለፉት 11 ወራት ያጋጠመው ችግር በማለት ለፓርላማው አባላት አስረድተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ለኮሚሽኑ ዕቅድ ማስፈጸሚያ ከመንግሥት የተፈቀደው የመደበኛ በጀት አነስተኛ ከመሆኑም በላይ፣ በየወሩ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የሚለቀቀው ወይም አንድ-አሥራ-ሁለተኛ የሚባለው አሠራር፣ በተለይም በኮሚሽኑ የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች አሠራር ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ ሌላው ኮሚሽኑን ያጋጠመው ተፅዕኖ እንደሆነ ኮሚሽነሩ  አስረድተዋል፡፡

በበጀት ዓመቱ ያጋጠሙት እነዚህ ችግሮች ቢኖሩም፣ ኮሚሽኑ ያከናወናቸው ተግባራት መኖራቸውን ኮሚሽነሩ አስረድተዋል፡፡ በዚህም ረገድ በአጠቃላይ የ2007 ዓ.ም. አምስተኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ ሕገ መንግሥቱን፣ የምርጫ ሕጎችንና ዓለም አቀፍ መሥፈርቶችን መሠረት ባደረገ ሁኔታ፣ የመምረጥና የመመረጥ መብቶችን ጨምሮ የዜጎች ሰብዓዊ መብቶችን ባከበረ መንገድ እንዲፈጸም ክትትል ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

የሴቶችና የሕፃናት መብትን ለማስጠበቅ እንዲቻል፣ በተለይም የመብት ጥሰት መንስዔ የሆኑትን ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና የግል ጥቃቶች ለመከላከል ብሎም ለማስወገድ የተጀመሩ ሕዝባዊ ንቅናቄዎችና መድረኮች እንዲጠናከሩ ኮሚሽኑ ያደረገው ድጋፍ እንዲሁ በበጀት ዓመቱ ከተከናወኑ ጠንካራ ክንውኖች መሀል የሚጠቀሱ መሆናቸውን ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል፡፡

ላለፉት አምስት ዓመታት ኮሚሽኑን በኮሚሽነርነት ሲያገለግሉ የነበሩት አባላት በአዲስ ለመተካት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኅብረተሰቡ የዕጩዎች ጥቆማ እንዲያደርግ ያስነገረ ሲሆን፣ በዚህም መሠረት በአዲሱ የፓርላማው የመጀመሪያ ዓመት  አዲስ ኮሚሽነር የሚመረጥ በመሆኑ፣ ይህ ሪፖርት በአምባሳደር ጥሩነህ አማካይነት የቀረበ የመጨረሻው ነው፡፡

 

የእነ አቶ መላኩ ፈንታ ክስ ለሁለተኛ ጊዜ የሕገ መንግሥት ትርጉም ጥያቄ አስነሳ

በቀድሞው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር በእነ አቶ መላኩ ፈንታ መዝገብ በከባድ ሙስና የተከሰሱ ነጋዴዎችና የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የጉምሩክ አዋጅ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይገባል ወይስ አይገባም በሚለው

ጉዳይ ላይ ለመወሰን፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ መንግሥት ትርጉም እንዲሰጥ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 15ኛ ወንጀል ችሎት ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉዳዩን መራለት፡፡

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክሱን መሠረት ያደረገው በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 411 (የመንግሥት ሥራን ለማያመች አኳኋን መምራት) እና በተሻሻለው የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 622/2001 ላይ ነው፡፡ ይሁንና አዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ቁጥር 859/2006 በቀድሞው ሕግ በወንጀልነት የተፈረጁ ድርጊቶችን የሚሽር ነው፡፡ ተከሳሾቹም ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡት ጥያቄ በኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 22(2) ላይ የወንጀል ክስ የቀረበበት ድርጊት ከተፈጸመ በኋላ የወጣ ሕግ ለተከሳሹ ጠቃሚ ሆኖ ከተገኘ፣ ከድርጊቱ በኋላ የወጣው ሕግ ተፈጻሚ እንደሚሆን ስለሚደነግግና የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 5(3)ም በተመሳሳይ ይኼንኑ የሚደነግግ በመሆኑ፣ በአዲሱ ሕግ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከተሻሩት አንቀጾች ነፃ እንዲወጡ ነው፡፡

ይኼን ጥያቄ ካቀረቡት ተከሳሾቹ መካከል አቶ መላኩ ፈንታ፣ አቶ ገብረ ዋህድ ወልደ ጊዮርጊስ (የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር)፣ አቶ ነጋ ገብረ እግዚአብሔር (የነፃ ትሬዲንግ ባለቤት)፣ አቶ ስማቸው ከበደ (የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባለቤት) እና ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ (የአዲስ ካርዲያክ ሆስፒታል መሥራችና ባለድርሻ) ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ፍቅር ማሩ የተከሰሱት ከመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመመሳጠር የሕክምና ዕቃዎችን በሕገወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ አስገብተዋል ተብለው ነው፡፡ በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ ይኼ ድርጊት በገንዘብ የሚያስቀጣ እንጂ፣ የወንጀል ድርጊት ባለመሆኑ ነፃ መውጣት እንዳለባቸው ተከራክረዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ግን ድርጊቱ ኮንትሮባንድ በመሆኑ ይኼ ድርጊት ግለሰቡን በወንጀል ከመጠየቅ አያድናቸውም ሲል ተከራክሯል፡፡ በተጨማሪም የወንጀል  ሕግ አንቀጽ 411 አሁንም እንዳልተሻረ አስታውሷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተከራካሪ ወገኖችን ክርክር ከሰማ በኋላ አዲሱ አዋጅ ተከሳሾቹን ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለውን ጭብጥ መርምሯል፡፡ ፍርድ ቤቱ በአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ በቀድሞው አዋጅ ወንጀል የነበሩ ድርጊቶች መሻራቸውን ማረጋጡን ገልጿል፡፡ ይሁንና በአዲሱ አዋጅ አንቀጽ 182 ላይ ‹‹በሌሎች ሕጎች የተደነገገው እንደተጠበቀ ሆኖ ይኼ አዋጅ ከፀናበት ቀን በፊት የተጀመሩ ጉዳዮች በነበረው ሕግ መሠረት ፍፃሜ ያኛሉ፤›› ተብሎ መደንገጉ ልዩ ሁኔታን እንደሚፈጥር አስገንዝቧል፡፡ የወንጀል ሕጉ ጠቅላላ ሕግ በመሆኑና የጉምሩክ አዋጅ ደግሞ ልዩ ሕግ በመሆኑ፣ በመርህ ደረጃ ልዩ ሕግ ከጠቅላላ ሕግ ቅድሚያ ተሰጥቶት ተግባራዊ እንደሚሆን አመልክቷል፡፡ ነገር ግን ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ሕግ በሕግነት ፀንቶ የማይቆም በመሆኑ፣ አዲሱ ሕግ ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚጣጣም ስለመሆኑ መመርመር እንደሚያስፈልግ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡

በፍርድ ቤቱ ዕይታ የአዲሱ የጉምሩክ አዋጅ አንቀጽ 182 በሕገ መንግሥቱ ከተቀመጡት አንቀጽ 9፣ 13 (ሕገ መንግሥቱ የበላይ ሕግ ስለመሆኑና ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚፃረር ማንኛውም ሕግና ውሳኔ እንደማይፀና ይደነግጋሉ) እና 22 ጋር የሚጣጣም ባይሆንም፣ ሕገ መንግሥቱን የመተርጎም ሥልጣን የሌለው በመሆኑ የዚሁ ሥልጣን ባለቤት የሆነው የፌዴሬሽን ምክር ቤት ጉዳዩን መርምሮ ሕገ መንግሥቱን በመተርጎም፣ ውሳኔውን ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. እንዲያቀርብ መርቶታል፡፡ 

ይኼው ክስ ከዚህ ቀደም ባስነሳው ሌላ ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የከፍተኛ የፌዴራል መንግሥት ባለሥልጣናት ጉዳይ በጠቅላይ ፍርድ ቤት የመጀመርያ ደረጃ ሥልጣን እንዲታይ የሚደነግገው አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀጽ 8(1)፣ በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠውን ይግባኝ የመጠየቅ መብት የሚጥስ ነው ተብሎ እንዲሻር ማድረጉ ይታወሳል፡፡

 

የቻይና መንግሥት ከፍተኛ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ የኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ትኩረት እንዲደረግ፣ ዝቅተኛና መካከለኛ ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ያደረጉ ፋብሪካዎች ደግሞ ተነቅለው ወደ አፍሪካ እንዲሄዱ ማዘዙ ተሰማ፡፡

ከአፍሪካ አገሮች በተለይ ግብፅና ኢትዮጵያ ተመርጠዋል፡፡ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ ዕድገት ይበጃሉ ያላቸውን ፋብሪካዎች ለመቀበል፣ ከቻይና ናሽናል ዴቨሎፕመንትና ሪፎርም ኮሚሽን ጋር ለመደራደር ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የቻይና መንግሥት ዝቅተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ከአገር ወጥተው እንዲሠሩ ውሳኔ ያሳለፈው፣ አገሪቱ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ያላትን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ከፍተኛ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ ፋብሪካዎች ላይ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል በማለቱ ነው ተብሏል፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪም በቻይና የአገልግሎት ዘርፍን ለማሳደግና ከዚህ ቀደም ርካሽ የነበረው የሰው ኃይል በአሁኑ ጊዜ እየተወደደ በመምጣቱ፣ ፋብሪካዎቹ ከአገር ወጥተው በማደግ ላይ ባሉት ኢትዮጵያና ግብፅ እንዲተከሉ መመርያ ማስተላለፉ ተነግሯል፡፡

ይህንን እንደ መልካም አጋጣሚ የተመለከተው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ ለአገሪቱ ዕድገት ወሳኝ የሚባሉ ፋብሪካዎችን በመምረጥና የቻይና መንግሥት ሊያቀርብ ስለሚችለው የፋይናንስ ሁኔታ ድርድር እንዲያደርግ፣ ኃላፊነቱን ለገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር መስጠቱ ታውቋል፡፡

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሱፍያን አህመድ የሚመሩት የልዑካን ቡድን በቅርቡ ወደ ቻይና ተጉዞ፣ ከቻይና ብሔራዊ ዴቨሎፕመንትና ሪፎርም ኮሚሽን ኃላፊዎች ጋር የመጀርያውን ድርድር ማካሄድ እንደሚጀምር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ 

የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከግብርና በማላቀቅ በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ መሠረት ላይ ለማሳረፍ ያቀደው የኢትዮጵያ መንግሥት በተለይ ለጨርቃ ጨርቅ፣ ለቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ ለብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ፣ ለስኳር ልማትና ለኬሚካል ኢንዱስትሪ ልማት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቷል፡፡

ይህንን ዕቅድ ለማሳካትም በዶ/ር አርከበ እቁባይ የሚመራው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን፣ በአሥር ቢሊዮን ዶላር ወጪ በተለያዩ ከተሞች የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በማቋቋም ላይ ይገኛል፡፡

ወደ ኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ እንዲቀላቀሉ የሚመረጡት የቻይና ፋብሪካዎች በእነዚህ የኢንዱስትሪ ዞኖች ውስጥ ወይም ራሳቸው በሚያቋቁሟቸው የኢንዱስትሪ ዞኖች ውስጥ ፋብሪካዎቻቸውን እንዲተክሉ እንደሚደረግ፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ዘርፍ ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶችን ለማምረት አመቺ መሆኑን ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ መንግሥት ኢንቨስትመንት በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ተዋናዮችን ለማረበታታት ያወጣቸው በርካታ ሕጎችና ማበረታቻዎች፣ እንዲሁም በአገሪቱ ያለው የሰው ኃይል አገሪቱን ተመራጭ ማድረጉን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

  

 

በቴክኒክና በንግድ ሥራ የሠለጠኑ 63 ሴቶች ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቁ፡፡ በሥልጠናው በወተትና የሥጋ ምርት አቅርቦት፣ እንዲሁም የቁም ከብት ንግድ ላይ ክህሎት የሚያሳድግ ግንዛቤ ማግኘታቸውን በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

ሥልጠናውን ያዘጋጀው የአሜሪካ መንግሥት በዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲው (USAID) ሲሆን፣ በ2004 ዓ.ም. በሴቶች ላይ በተደረገ ጥናት በወተት ምርት፣ በእንስሳት ዕርባታ፣ በአመራር ዕውቀት፣ በንግድ ሥራ አገልግሎቶች ተደራሽነት፣ ውሳኔ በመስጠት፣ በስኬታማ የንግድ ሥራ ዕቅድ አዘገጃጀት ረገድ የታዩትን ክፍተቶች ለመሙላት ነው ተብሏል፡፡ 

የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ኤጀንሲ ‹‹ወደፊትን መመገብ›› በተሰኘ ፕሮግራሙ በግብርና ዕድገት ፕሮግራም የእንስሳት ገበያ ልማትና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ በሚያስችል አቅም መመረቅ በተሰኙ መርሐ ግብሮች፣ በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ሥልጠና ሰጥቷቸዋል፡፡ በሥልጠናው የተካተቱት ሴቶች የሥራ ፈጠራ አቅም እንዳላቸው የታመነባቸው መሆናቸው በመግለጫው ተመልክቷል፡፡ ሴቶቹ በአስተዳደርና በሥራ አመራር ክህሎት ሥልጠና የተሰጣቸው ሲሆን፣ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያግዝ የንግድ ሥራ ዕቅድ በመንደፍ ረገድም የቴክኒክ ዕውቀት ማግኘታቸው ተገልጿል፡፡

ሠልጣኞቹ ከአማራ፣ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል እንዲሁም ከትግራይ ክልል የተውጣጡ ናቸው፡፡ በቆይታቸው ያገኙትን ክህሎት በአካባቢያቸው ለሚገኙ ሴቶችም እንደሚያካፍሉ ይጠበቃል፡፡

ሴቶች በእንስሳት ዕርባታና በእንስሳት ምርት አያያዝ የሚጫወቱትን ሚና ማሳደግ ለቤተሰብም ሆነ በአገር ደረጃ ከፍ ያለ ጠቀሜታ አለው ያሉት የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ ተወካይ ካለን ሒዩስ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት በንግድ ሥራ አስተዳደርና በአመራር ላይ ያተኮረው ሥልጠና፣ በእንስሳት ዕርባታ ዕምቅ አቅም ያላቸው አርዓያ ሴቶች ላይ ማተኮሩ፣ በዘርፉ የመሪነቱን ሚና እንዲጫወቱ ያግዛቸዋል፡፡ በሥልጠናው ያልተካተቱ ሴቶችም በሠልጣኞቹ አማካይነት ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል፡፡ 

 

መንግሥት የፓርቲዎቹን መግለጫ ውድቅ አድርጓል

በአንድ ቀን ልዩነት የአረና/መድረክ እና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በተለያዩ ሥፍራዎች ተገድለው በመገኘታቸው ምክንያት ሰማያዊ ፓርቲና አረና/መድረክ በመንግሥት ላይ ወቀሳ አቀረቡ፡፡

ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. በአማራ ክልል በምሥራቅ ጎጃም ዞን በደብረ ማርቆስ ከተማ አቶ ሳሙኤል አወቀ የተባሉ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ ሲገደሉ፣ በማግሥቱ አቶ ታደስ አብረሃ የተባሉ የአረና/መድረክ አባል በትግራይ ክልል ምዕራብ ዞን ማይካድራ ከተማ  መገደላቸውን ሁለቱም ፓርቲዎች አስታውቀዋል፡፡

አረና/መድረክ ባወጣው መግለጫ አባሉ በምዕራብ ትግራይ ዞን የድርጅቱ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው በ2007 ምርጫ ወቅት፣ የፓርቲውን ሥራ በማደራጀትና በማንቀሳቀስ ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ የቆዩ መሆናቸውን፣ ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት ለጊዜው ባልታወቁና ቤታቸው በመጡ ሦስት ሰዎች ግድያ እንደተፈጸመባቸው አስታውቋል፡፡

ፓርቲው የገዳዮቹን ማንነት አለመታወቁን በጠቆመበት መግለጫ፣ ሟች አባሉ ከግድያው ቀደም ብሎ በመንግሥት የፀጥታ ሠራተኞች ወከባና ማስፈራርያ ይደርስባቸው እንደነበር ጠቁሟል፡፡

‹‹ለጉዳተኛው የሕክምና ዕርዳታ እንዲደረግላቸው ለማስተባበርና ወንጀለኞችም ለመከታተልና ለማስያዝ የተደረገው ሙከራ በፖሊሶች አለመተባበር›› ሳይሳካ መቅረቱን በመግለጫው አረና/መድረክ አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይም ሰማያዊ ፓርቲ አቶ ሳሙኤል የተባሉ አባሉ ከመገደላቸው በፊት፣ በደኅንነት ሠራተኞችና በአካባቢው ሹሞች የግድያ ማስፈራርያ ይደርሳቸው እንደበር ገልጿል፡፡

የምሥራቅ ጎጃም ዞን ፖሊስ መምርያ በበኩሉ አቶ ሳሙኤል በሁለት ግለሰቦች መገደላቸውን ገልጾ፣ አንደኛው ተጠርጣሪ በቁጥጥር ሥር ውሎ ሲመረመር ግድያውን መፈጸሙን ማመኑን አስታውቋል፡፡

ነገር ግን የፖሊስን መግለጫ ሙሉ በመሉ ውድቅ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ‹‹የሰማዕታት ደም ይጮሃል፣ ይጣራል›› በሚል ርዕስ ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹ይህ ሥርዓት በሕግም፣ በሞራልም ኢትዮጵያን የማስተዳዳር ብቃት የለውም፡፡ ወንጀለኞችን ለፍርድ ይቅረቡ እያልን አናላዝንም፣ ወንጀለኞቹ የመንግሥት አካላት ናቸውና፤›› ሲል መንግሥትን ምንም ዓይነት ፍትሕ እንደማይጠብቅም ገልጿል፡፡

እንዲሁም አረና/መድረክ በበኩሉ በትግራይ ክልል ከ17 በላይ አባላት ጨምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራና በደቡብ ክልሎች በአባላት ላይ እስራት፣ ግርፋትና ግድያ እየተፈጸመባቸው መሆኑን በመግለጫው አስፍሯል፡፡

መንግሥት በበኩሉ ክሶቹን ውድቅ በማድረግ ተገደሉ በተባሉት ሰዎች እጁ እንደሌለበት ገልጾ፣ ትችቶቹ ሁሉ እውነትነት የሌላቸው መሆኑን አስታውቋል፡፡

በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሽመልስ ከማል፣ ‹‹ሁለቱም የተቃዋሚዎች አባላት በግለሰቦች መገደላቸውንና ጉዳዮችን ይዞ ለፍርድ ለማቅረብ ፖሊስ ምርመራውን ቀጥሏል፡፡ መንግሥት እንደሚያምነው የሁለቱ ዜጎች መገደል ምንም ዓይነት ፖለቲካዊ ይዘት የለውም፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በተለይ የሰማያዊ ፓርቲ አባል ግድያ አሳዛኝ እንደሆነ፣ ሟች ከቀድሞ ደንበኞቹ ጋር በተፈጠረው አለመግባባት መገደሉን ፖሊስ አረጋግጧል  ካሉ በኋላ፣ አቶ ታደሰ በማይታወቁ ሰዎች ከመገደላቸውና ፖሊስ ምርመራ እያደረገ መሆኑን ከማወቃቸው ውጪ፣ ገና መረጃው እንዳልደረሳቸው አቶ ሽመልስ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የአረና/መድረክ አባልን ግድያ በተመለከተ የትግራይ ክልል የፀጥታና የደኅንነት ቢሮን ምላሽ ለማግኘት ሪፖርተር ተደጋጋሚ ጥረት ቢያደርግም፣ ኃላፊዎችን በስብሰባ ምክንያት ለማግኘት ባለመቻሉ አስተያየታቸውን ማካተት አልተቻለም፡፡ 

 

የ120 ሚሊዮን ዶላር የኃይል ማስተላለፊያ መስመር ግንባታ ስምምነት ተፈረመ

ኢትዮጵያና ኬንያን በኤሌክትሪክ ኃይል ለማገናኘት፣ በኢትዮጵያ በኩል የ433 ኪሎ ሜትር ኃይል ማስተላለፊያ መስመር መገንባት የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ፡፡ ስምምነቱ ሰኔ 12 ቀን 2007 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል

አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀና ግንባታውን ለማካሄድ የተመረጠው የቻይናው ስቴት ግሪድ እህት ኩባንያ ሲኢቲ ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ሚስተር ቸንግ ዊ በሸራተን አዲስ ተፈራርመዋል፡፡ የኃይል መስመሩ አንደኛው ኮንትራት በ120 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የሚገነባ ሲሆን፣ ወጪው በአፍሪካ ልማት ባንክ ይሸፈናል ተብሏል፡፡ ግንባታው ከወላይታ ሶዶ ተነስቶ ኬንያ ድንበር ሞያሌ ላይ የሚቆም ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ያለውን 612 ኪሎ ሜትር የኃይል መስመር ኬንያ ትገነባለች፡፡ ኢትዮጵያ 400 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለኬንያ ለመሸጥ ስምምነት ያረገች በመሆኗ፣ አንዱን ኪሎ ዋት በሰባት የአሜሪካ ሳንቲም ለመሸጥ ስምምነት ተደርጓል፡፡

የቻይናው ኩባንያ የፈረመው በኢትዮጵያ በኩል ከሚገነቡት ሁለት ኮንትራክተሮች መካከል አንዱ ሲሆን፣ በቅርቡ አንደኛው ኮንትራት ይፈረማል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በኬንያ በኩል የሚገነባው የኃይል መስመር በሦስት ኮንትራቶች የተከፈለ ነው፡፡ ግንባታውን ለማካሄድ አሸናፊ ከሆኑ የህንድ ኩባንያዎች ጋር በቅርቡ ስምምነት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህ ግንባታ በ26 ወራት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሏል፡፡ የቻይናው ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንትም ግንባታው በተያዘለት ጊዜ ገደብ እንደሚጠናቀቅ ቃል ገብተዋል፡፡ በምሥሉ ላይ ኢንጂነር አዜብ አስናቀና የቻይናው ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ቸንግ ዊ ስምምነቱን ከተፈራረሙ በኋላ፡፡

 

የመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ባለፉት 11 ወራት አርባ ያህል ከፍተኛ ኪሳራ ሊያስከትሉ የሚችሉ የሳይበር (ኮምፒዩተርን መሠረት ያደረጉ) ጥቃቶችን ማምከኑን፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታወቀ፡፡

ኤጀንሲው ከተቋቋመ በርካታ ዓመታት ቢያልፉም፣ እንደ አዲስ በተነደፈው አሠራር መሠረት ለመጀመርያ ጊዜ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምክር ቤቱ አቅርቧል፡፡

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል ተክለ ብርሃን ወልደ አረጋይ እንደገለጹት፣ የአገሪቱን ቁልፍ መሠረተ ልማቶች ለማጥቃት የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች ነበሩ፡፡

‹‹ወደ አገራችን የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶች በርካታና ብዙ መልክ  ያላቸው ናቸው፤›› ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ‹‹አንዳንድ የጥቃት ዓይነቶች አገራችንን በተለየ ሁኔታ ዒላማ ያላደረጉ ነገር ግን ማንኛውም ተጋላጭ መሠረተ ልማትን የሚያጠቁ ሲሆን፣ እንደዚህ ዓይነት ጥቃቶች በየቀኑ ከዚህ አልፎም በየሰዓቱ የሚሠራጩ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

ሌሎች ሆን ተብሎ የኢትዮጵያን የሳይበር መሠረተ ልማት ለማጥቃት የሚለቀቁ ቫይረሶች መኖራቸውን የገለጹት ሜጀር ጄኔራል ተክለ ብርሃን፣ ወደ አርባ የሚጠጉ በአጠቃላይ መሠረተ ልማቱንና የተወሰኑ ቁልፍ ተቋማትን ዒላማ ያደረጉ ከፍተኛ ኪሳራ ሊያደርሱ የነበሩ የሳይበር ጥቃቶችን ለማምከን መቻሉን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ጥቃቱ ቢደርስ ኖሮ ሊያስከትል የነበረው ኪሳራ በጣም ትልቅ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ ከዚህ ውጪ የሳይበር ጥቃቶቹ በየትኞቹ ቁልፍ ተቋማት ላይ እንደተሠነዘሩ፣ እንዲሁም ከየት አካባቢ እንደሆነ አልገለጹም፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪ በቴሌኮም ማጭበርበር ተግባር ላይ የተሰማሩ 55 ተጠርጣሪዎች በሕግ ቁጥጥር ሥር መዋላቸውን፣ ለዚህ የወንጀል ተግባር ሲጠቀሙባቸው የነበሩ ወደ 170 የተራቀቁና ዘመናዊ ሕገወጥ የቴሌኮም መሣሪያዎች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡ ግለሰቦቹ በቴሌኮም ወንጀል ተሰማርተው በነበረበት ወቅት 700 ሚሊዮን ብር ኪሣራ በኢትዮ ቴሌኮም ላይ ማድረሳቸውንም ተናግረዋል፡፡

ኤጀንሲው የተሰጠውን ተልዕኮ በተቀናጀና በተጠናከረ መንገድ ለመወጣት እንዲችል ቀደም ሲል የተጀመረውን በዘርፉ ያሉትን የሕግ፣ የፖሊሲና የስታንዳርድ ክፍተቶች በመለየት ክፍተቶችን ለመዝጋት እየሠራ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡

ከእነዚህም መካከል የሳይበር ወንጀል ሕግ ረቂቅ ማዘጋጀት አንዱ ሲሆን፣ በ2005 ዓ.ም. ለካቢኔ ቀርቦ የነበረ ነው፡፡ ረቂቅ ሕጉ ከፍትሕ ሚኒስቴር ጋር በመሆን እንደገና እንዲታይ በመወሰኑ በድጋሚ በመታየት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

  

እስራኤላዊው ምሁር ከስደት ተመላሽ ወገኖች አክራሪነት እንዳላጠላባቸው እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል አሉ

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥርጣሬውን አጣጥሏል

በዓለም አቀፍ የፀረ ሽብር ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪና በእስራኤል መንግሥት የዲፕሎማሲና የስትራቴጂ ተዛምዶ ማዕከል አማካሪ የሆኑት ዶ/ር ዮናታን ፋይን፣ ኢትዮጵያ ከስደት የምትመልሳቸው ዜጐቿ ከአክራሪነት ጥላ የራቁ መሆናቸውን

ማረጋገጥ እንደሚገባት አሳሰቡ፡፡ የደኅንነትና ዓለም አቀፍ ጥናት ምሁሩ ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት ከየመን፣ ከሊቢያና ከሌሎችም የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ወደ አገር ቤት በሚመለሱ ዜጐች ላይ መንግሥት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡

ዓለም አቀፍ የሽብር ቡድኖችና ጽንፈኛ እምነትን የሚያራምዱ ግለሰቦችና ድርጅቶች በሞሉባቸው የመካከለኛው ምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ አገሮች በብዛት የሚገኙት ኢትዮጵያውያን፣ በአንድም ሆነ በሌላ አጋጣሚ በእነዚህ አካላት ተፅዕኖ ሥር ወድቀው ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡ ይህም እነዚህ ወገኖች ወደ አገራቸው ገብተው ከሚገጥሙዋቸው የመልሶ መዋሀድ ተግዳሮቶች ጋር ተዳምሮ ላልተፈለገ የባህርይ ለውጥ ሊዳርጋቸው እንደሚችል ምሁሩ ገልጸዋል፡፡

ይህ ጥርጣሬ ለምን እንደገባቸው ተጠይቀው የመለሱት ምሁሩ፣ በተለያዩ የዓለም አገሮች የተደረጉ ጥናቶች የሚያሳዩት መረን ላወጣ አፈንጋጭነትና አክራሪነት እርሾ የሚሆኑት ባህርያት በሆነ ወቅት ወደ አገር ቤት ተመልሰው መኖር በሚጀምሩ ዜጎች ምክንያት የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ በተለይ በርካታ ዜጐቿን በስደት የምታጣው አፍሪካ ዜጎቿ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች ከሚገጥማቸው የኑሮ ውጣ ውረድ ጋር ተዳምሮ፣ ለአዳዲስና የኑሮ ሁኔታን ሊቀይሩ ይችላሉ ለተባሉ አስተሳሰቦች በቀላሉ የመንበርከክ ዕድል እንዳላቸውም ገልጸዋል፡፡ በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በምዕራብና በመካከለኛው አፍሪካ የሚገኙ በርካታ ዜጐች በእነዚህ አዳዲስ አስተሳሰቦች በመማረካቸው ምክንያት ወደ አገራቸው ሲመለሱም ይህንኑ አቋማቸውን እንደሚገፉበት ምሁሩ ያስረዳሉ፡፡

እስራኤላዊው ምሁር እስካሁን ድረስ በኢትዮጵያ የሚታየው ሁኔታ በዚህ ደረጃ የሚጠቀስ አለመሆኑን፣ የሕዝቡ የረጅም ዘመናት ተቻችሎ የመኖር ልማድ ለዚህ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን እንደሚያምኑ ገልጸው፣ ነገር ግን ይህ ሁኔታ በተለያዩ የውጭ ተፅዕኖዎችና አካባቢያዊ ሁኔታዎች ሊሸረሸር እንደሚችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ለዚህም ኢትዮጵያ የምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋትና ለአደገኛ ቡድኖች አመቺ ሥፍራ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ 

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ፣ የምሁሩ አስተያየት ምንም መሠረት የለውም ባይባልም ዓለም አቀፋዊ ገጽታን የተላበሰ መሆኑን በመጠቆም፣ ለጊዜው ግን ሥጋትን የሚያጭር አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህንን ጉዳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በቀጥታ ባይመለከተውም፣ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ተገቢውን ሥራ እንደሚያከናውን እገምታለሁ፡፡ በእኛ በኩል ከየትም አገር የሚመጣ ዜጋ በኤምባሲዎችና በቆንስላዎች አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ ሲያሟላ እናስተናግዳለን፤›› ሲሉ አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀዳሚ ዓላማም የዜጐችን ማንነትና ምንነት ማጥናት ሳይሆን፣ የነፍስ አድን ተግባሩን በማቀላጠፉ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ 

እንደ ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አይኦኤም መረጃ፣ በየመን ብቻ ከ50 ሺሕ በላይ ኢትዮጵያውያን መኖራቸው ሲታወቅ እስካሁን ድረስ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸው ታውቋል፡፡ በሊቢያ የሚገኙ ዜጐችም በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆናቸውንም የድርጅቱና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጀመረውን የነፍስ አድን ዘመቻ አጠናክሮ እንደሚቀጥልበት፣ በየትኛውም አገር የሚገኝ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ሊጠቀምበት የሚችል ዕድል መሆኑንም አቶ ተወልደ ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በእስራኤል የሚገኙ ቤተ እስራኤላውያንን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ምንም የቀረበ ጥያቄ አለመኖሩን፣ ጥያቄው ከቀረበ ግን እነሱንም ለመርዳት መንግሥት ዝግጁ መሆኑን አቶ ተወልደ አስታውቀዋል፡፡

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን ለሪፖርተር ያጋሩት እስራኤላዊው ምሁር ዶ/ር ዮናታን፣ ኢትዮጵያውያኑ ቤተ እስራኤላውያን በእስራኤል እየገጠማቸው ያለው ፈተና አሳሳቢ መሆኑን፣ በአንዳንድ ምግባረ ብልሹ የፀጥታ ኃይሎች የሚፈጸመውን ጥቃትም አጥብቀው የሚቃወሙ በርካታ እስራኤላውያን መኖራቸውን በመጠቆም፣ የቤተ እስራኤላውያኑ የመብት ጥያቄዎች ሁሉ ምላሽ ሊያገኙ እንደሚገባቸው አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ይህ የዘር መድልኦ ዛሬም ድረስ በአሜሪካና በሌሎችም ያደጉ አገሮች የሚስተዋል በመሆኑ፣ የእስራኤልን ሁኔታ አዲስ አያደርገውም፡፡ ከዚህ በፊት ሩሲያውያንን ጨምሮ ሌሎችም ትውልደ እስራኤላውያን በተመሳሳይ ችግር ውስጥ አልፈው እዚህ በመድረሳቸው፣ ቤተ እስራኤላውያኑም በቅርብ ጊዜ ችግራቸው እንደሚፈታ እገምታለሁ፤›› በማለት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተደጋጋሚ የሚከሰተውን የቤተ እስራኤላውያን ቁጣና የእስራኤል ባለሥልጣናትን ዘገምተኛ የመፍትሔ ዕርምጃ ገልጸውታል፡፡