አፈንዲ ሙተቂ

የስራ ግዴታዬ ሆኖ ከህዳር ወር 2007 (November 2014) ጀምሮ በመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ታሪክ ዙሪያ የተጻፉ ሰነዶችን እየመረመርኩ ነው፡፡ በዚህም ድሮ የማላውቃቸውን አስደናቂና አስገራሚ ታሪኮች ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ለረጅም ጊዜ እንቆቅልሽ ሆነው ሲያስቸግሩኝ ለነበሩት ጉዳዮችም ምላሽ አግኝቻለሁ፡፡ ለብዙ ዓመታት ስፈልጋቸው የነበሩትን ምርጥ መጻሕፍትንም አግኝቼ ይዘታቸውን በቅርበት ለማወቅ ችያለሁ፡፡

 

ታዲያ በዚህ ምርመራዬ ያስተዋልኳቸው ሌሎች ጉዳዮችም አሉ፡፡ ከነርሱም አንዱ አንዳንድ ጮሌዎች ታሪክን በመጻፍ ስም ፖለቲካን የሚያሸከረክሩበት ጥበብ ነው፡፡ ለዚህ ዋቢ ይሆነኝ ዘንድ የአንድ ሀገር ዜጋ የሆኑ ሁለት ምሁራንን ልጥቀስ፡፡

—-

ሞርዴኻይ አቢር (Mordechai Abir) የሚባል ስም ታውቃላችሁ?…. አዎን! ስለ “ዘመነ መሳፍንት” የተጻፉ ጽሑፎችን ያነበበ ሰው “አቢር” የሚለውን ስም በደንብ ያስታውሳል፡፡ እኝህ ሰው የቀድሞው “ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ዩኒቨርሲቲ” (የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) የታሪክ ፕሮፌሰር ነበሩ፡፡ ደርግ ስልጣን ከተቆጣጠረ በኋላ ደግሞ ወደ እስራኤል በመጓዝ በኢየሩሳሌም በሚገኘው የሂብሩ ዩኒቨርሲቲ መምህርነት አገልግለዋል፡፡ አቢር “The Era of Princes” በሚል ርዕስ የጻፉት መጽሐፍ በምሁራን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት አለው፡፡ እኔም በአንድ ወቅት (የዛሬ አስር ዓመት ገደማ) መጽሐፉን አንብቤው ነበር፡፡

 አቢር በጣም ዝነኛ የሆነ ሌላ መጽሐፍም አላቸው፡፡ ርዕሱ “Ethiopia and the Red Sea” ይሰኛል፡፡ በየትኛውም ወገን ሆኖ ስለኢትዮጵያ ታሪክ የሚጽፍ ሰው ይህንን መጽሐፍ እየደጋገመ ይጠቅሳል፡፡ ታደሰ ታምራት፣ ሪቻርድ ፓንክረስት፣ ነጋሶ ጊዳዳ፣ መርዕድ ወልደ አረጋይ፣ ሙሐመድ ሐሠን፣ ላጵሶ ድሌቦ፣ ኡልሪች ብራውኬምፐር፣ አባስ ሐጂ ገነሞ፣ አሌሳንድሮ ጎሪ እና ሌሎችም ፕሮፌሰሮች የአቢርን መጽሐፍ እንደ ምንጭ ይጠቀሙበታል፡፡ ሰለሰሜን ኢትዮጵያም ሆነ ስለደቡቡ ክፍል በተጻፈ መጽሐፍ ውስጥ “Abir” የሚለውን ስም በግርጌ ማስታወሻ እና በመጽሐፉ ማጣቀሻ ክፍል ውስጥ ማየት የተለመደ ነው፡፡ ነገር ግን “Ethiopia and the Red Sea”ን ለረጅም ጊዜ አይቼው ስለማላውቅ በምሁራን ዘንድ ተመራጭ የሆነበትን ምክንያት ለመረዳት ስቸገር ቆይቻለሁ፡፡ ዘንድሮ ግን ፈጣሪ ብሎልኝ  አግኝቼዋለሁ፡፡  ብዙ ጊዜ እየመላለስኩ ካየሁት በኋላም መጽሐፉ በምሁራን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኘበትን ምክንያት ለመረዳት ችያለሁ!!

አዎን! ፕሮፌሰር አቢር ከልቡ ምሁር ናቸው፡፡ እውነተኛ ምሁር! መጽሐፋቸውን ያጠናቀሩት በእውነተኛ ምሁራዊ መንገድ ነው፡፡ ብዙዎችን እንቅ አድርጎ ሊያሰምጣቸው የሚታገላቸው ኢ-ምሁራዊ ሸፍጥና ውንብድና በመጽሐፋቸው ውስጥ የለም፡፡ አድሎ፣ መረጃ ማምታታት፣ የተወላገደ እይታ፣ ማስመሰል፣ መሸፈጥ ጂንኒ ጀቡቲ በመጽሐፉ ውስጥ አይታዩም፡፡ በመሆኑም “Ethiopia and the Red Sea” በህይወቴ ከገጠሙኝ አጃዒበኛ መጻሕፍት መካከል አንዱ አድርጌ መዝግቤዋለሁ፡፡ እውቀትን መገብየት ለሚሻ ሰው ግሩም መማሪያ ነው፡፡ ለተመራማሪዎችና ለተማሪዎች እጅግ በጣም አስፈላጊ የሆነ ማጣቀሻ ነው፡፡

ፕሮፌሰር አቢር በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ስድስት መጻሕፍትን ጽፈዋል፡፡ ሁሉም መጻሕፍት በምሁራን ዘንድ ከፍተኛ ከበሬታ አላቸው፡፡ ከነርሱ መካከል ከላይ የጠቀስኳቸው ሁለት መጻሕፍት የዓለማችን ቁጥር አንድ ኢንሳይክሎፒዲያ በሆነው “ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ” ቀዳሚ የማጣቀሻ ምንጮች በመሆን recommend ተደርገዋል፡፡

                       

ፕሮፌሰር አቢር እስራኤላዊ ናቸው፡፡ ታዲያ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ምርምር ሲያደርጉ የነበሩት እስራኤላዊ እሳቸው ብቻ አልነበሩም፡፡ ሌሎችም በዘርፉ ብዙ ስራዎችን አቅርበዋል፡፡ ከነርሱም አንዱ ሀጋይ ኤልሪክ ነው፡፡ “ሐጋይ ኤርሊክ” የሚለውን ስም ካወቅኩ አስራ አምስት ዓመታት አልፏል፡፡ ነገር ግን ከመጽሐፎቹ ያነበብኩት Ethiopia and the Middle East የሚል ርዕስ ያለውን ብቻ ነው፡፡ ሀጋይ ከመጽሐፎቹ ይልቅ በሴሚናሮችና ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶች ላይ የሚያቀርባቸውን በርካታ አጫጭር ጽሑፎችን ነው ያነበብኩት፡፡ ከህዳር 2007 ወዲህ ባለው ጊዜ ውስጥ ግን ሶስት ያህል መጽሐፎቹን አይቼለታለሁ፡፡ እናም አጃዒብ አልኩ!!

  ይገርማል!! ፕሮፌሰር ሃጋይ አወዛጋቢ ሰው ሆኖ ብቅ ያለው በቅርብ ዘመናት በሚጽፋቸው ጽሑፎቹ ይመስለኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ሰውየው ከመነሻው ጀምሮ የተወላገደ እይታ ያለው መሆኑን ነው ያስተዋልኩት፡፡ ምሁራዊ ውንብድና በመጽሐፎቹ ውስጥ እግሩን አንሰራፍቷል፡፡ ከሀጋይ መጽሐፍ ፖለቲካ እንጂ አንዳች የታሪክ እውቀት አይጨበጥም፡፡ ደግሞም የብዙዎቹ መጻሕፍት ጭብጥ “ኢትዮጵያ ራሷን ካልጠበቀች በሙስሊም አክራሪዎች ልትዋጥ ትችላለች” የሚል ነው፡፡ ባጭሩ “ሃጋይ” የእስራኤሉ ሞሳድ በኛ ላይ የተከለው የማስፈራሪያ ሳይኮሎጂስት እንጂ የታሪክ ምሁር ሆኖ አልተገኘም፡፡

በጣም የሚገርመው ደግሞ ሃጋይ ሌሎች ፀሐፊዎችን የሚፈርጅበት ድፍረቱ ነው፡፡ አንድን ክስተት ከርሱ በተለየ አኳኋን ለጻፉ የታሪክ ምሁራን በቶሎ ስም ያወጣላቸዋል፡፡ ሰውዬው ክርስቲያን ከሆነ “ኮሚኒስታዊ አስተሳሰብ ስላለው ነው” ይለዋል፡፡ ሙስሊም ምሁራንን ደግሞ ሁለት ሰሞችን ይሸልማቸዋል፡፡ ጸሐፊው የመካከለኛው ዘመን ሰው ከሆነ “Fanatic writer” ይለዋል፡፡ ፀሐፊው የዘመናችን ሰው ከሆነ ግን “Radical Islamist writer” ይለዋል፡፡ ከርሱ የሚቃረን ትርክት የጻፉ ሰዎችን እንዲህ ብሎ በሚፈርጅ ሰው የተጻፈ መጽሐፍ የታሪክ ማጣቀሻ የሚሆንበት አግባብ በጭራሽ የለም፡፡

የሀጋይ የላሸቀ ምሁራዊ በዚህ ብቻ የተገታ አይደለም፡፡ የታሪክ መረጃዎችን ለራሱ እንደሚመቸው እየገለባበጠ ይጽፋል፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ቁርኣን የአማርኛ ትርጉም በብዙ ምሁራን ተሳትፎ የተከወነ ሆኖ ሳለ (ዋነኞቹ ተርጓሚዎች ሼኽ ሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅ እና ሃጂ ሙሐመድ ሣኒ ሐቢብ ቢሆኑም) እርሱ ግን “ትርጉሙን ያከናወኑት ሃጂ ዩሱፍ ዐብዱራሕማን ነው” ይለናል፡፡ ሀጋይ እንዲህ የሚለው ሃጂ ዩሱፍን ለማድነቅ እንዳልሆነ ልብ በሉ፡፡ ይህንንም ትረካ የፈጠረው እርሱ በአድናቆት አቅሉን የሚስትላቸው ሼኽ ዐብዱላሂ ሙሐመድ (ዐብዱላሂ አል-ሐበሺ) በ1948 ከኢትዮጵያ የተባረሩት ሃጂ ዩሱፍ ዐብዱራሕማን በዶለቱት ሴራ ነው በሚል ለሚዘበዝበው ትረካ እንደማስረጃ ለመጠቀም ፈልጎ ነው፡፡ አንባቢያን “ሃጂ ዩሱፍ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤን አባብለው ሼኽ ዐብዱላሂ ከሀገር እንዲጠፉ የማድረግ አቅም ነበራቸው እንዴ” ብለው ሲጠይቁ የሃጋይ ኤርሊክ ጽሑፍ “ሰውዬው እንዲያ ማድረግ ይቅርና በቅቤ ምላሳቸው ንጉሡን በማሳመን ቅዱስ ቁርኣን እንዲተረጎም ያደረጉ ሼኽ ነበሩ” የሚል መልስ ይሰጣቸዋል ማለት ነው፡፡ ይህቺ ነች ዘዴ!! ይህቺ ነች ሸፍጥ!!

በሌላ በኩል ሃጋይ ኤርሊክ በቀጥታ ጠብ ጫሪነትን የሚያንጸባርቁ ጽሑፎችንም ይጽፋል፡፡ ለምሳሌ የሃጋይ አንዱ ጽሑፍ “The Grandchildren of Abraha” የሚል ርዕስ አለው፡፡ አብረሃ ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በተወለዱበት ዘመን የመንን ሲገዛ የነበረው የአክሱም ንጉሥ እንደራሴ ነው፡፡ ታዲያ ሀጋይ በዚህ ጽሑፍ የአሁኖቹን የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ መሪዎች “የአብረሃ የልጅ ልጆች ናቸው” ይላቸውና “እነዚህ ጀግኖች የተስፋፊውን የአክራሪውን የእስልምና ጂሃዲስቶች ድባቅ መምታት ይችላሉ” የሚል እድምታ ያለው ትረካ ይተረትራል፡፡ አብረሃ የጥንቱ የአክሱም ንጉሣዊ ግዛት ተወላጅ እንደነበረ ማንም አይክድም፡፡ ይሁን እንጂ የዛሬዎቹን የኢትዮጵያ ገዥዎች የአብረሃ ዝርያዎች ማለትም ሆነ የጥንቷ አክሱም ሌጋሲ አስቀጣይ አድርጎ ማቅረብ ስህተት ነው፡፡ የጥንቷ አክሱም በማህበራዊ ስብጥሯ ህብረ-ብሄር እንጂ የአንድ ብሄር ሀገር አልነበረችም፡፡ ግዛቷ ደግሞ ከትግራይ ባሻገር ኤርትራን፣ ሰሜን ምስራቃዊ ሱዳንና አብዛኞቹን የሰሜን ኢትዮጵያ ክልሎች ይጠቅላል፡፡  አብረሃ ከነዚህ ሁሉ ግዛቶች በየትኛው እንደተወለደ በትክክል አይታወቅም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ የዘመናችን የኢትዮጵያ መሪዎች የጥንቱ አብረሃ ሌጋሲ ወራሾች ናቸው የሚያስብል የታሪክና የአንትሮፖሎጂ ማስረጃ የለም፡፡

  

 የጽሑፉ አደገኛነት ግን ይህ አይደለም፡፡ የሃጋይ ምሁራዊ ሸፍጥ የሚያስከፋው ጥንት የተፈጸመን ታሪክ አሁን ካለው ጂኦ-ፖለቲካዊ ትርምስ ጋር እየቀላቀለ የጠብ ጫሪነት ስሜትን ለማንገሥ በመጣሩ ነው፡፡ የታሪክ ምሁር ዋነኛ ግብ የሰው ልጆች ትናንት የፈጸሟቸው ስህተቶችን እንዳይደግሙ ማስተማር እና ድሮ የነበራቸውን በጎ የአዕምሮና የማቴሪያል እሴቶችን ጠብቀው ወደ ቀጣዩ ትውልድ እንዲያስተላልፉ ማስቻል ነው፡፡ ሀጋይ ግን ታሪክን ሸርና ብጥብጥን ለማውረስ ሲል ብቻ የሚጠቀምበት ነው የሚመስለው፡፡

—-

ከላይ የጠቀስኳቸው ሁለት ምሁራን (ሞርዴኻይ አቢር እና ሀጋይ ኤርሊክ) ይሁዲዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን ሁለቱም የተለያየ ምሁራዊ ልቀትና ርትእ ያላቸው ሆነው ተገኝተዋል፡፡ ምሁራን “የአቢርን መጽሐፍ ማንበብ አለብህ” እያሉ ሲናገሩ የነበሩት “በአቢር መጽሐፍ ውስጥ እውቀት አለልህ” ማለታቸው እንደሆነ ገብቶኛል፡፡  ሀጋይ ኤርሊክ ግን በታሪክ ስም ጽዮናዊ ፖለቲካውን የሚያሰራጭ ሸፍጠኛ ነው እንጂ የምሁር “ኳሊቲ” የለውም፡፡

አንድ ነገር ግን አለ፡፡ ይሁዲ በሙሉ መጥፎ ነው የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ስህተት ነው፡፡ በጣም ስህተት!! ይህ የአዶልፍ ሒትለርና የመሰሎቹ አስተሳሰብ ነው እንጂ የጤናማ ሰው አስተሳሰብ አይደለም፡፡ አይሁድ በሙሉ መጥፎ እንዳልሆነ ለመረዳት የሚሻ ሰው የፕሮፌሰር አቢርን መጽሐፍ ብቻ ማንበብ ይበቃዋል፡፡ የህዝብን አንድነት የሚያናጉትን እንደ ሀጋይ ኤርሊክ ዓይነቶቹን መሰሪ ጸሐፊዎች ግን ጠንቀቅ በሏቸው፡፡ 

—–

First written on August 13/2015
Re-written on January 19/2016

ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

——

ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ያስተማሩት ትምህርት ዘመናዊነትን ይከለክላል?…. በዘመን አፈራሽ የቴክሎኖጂ ትሩፋቶችና በተቀላጠፉ አሰራሮች መጠቀምን እርም ያደርጋል?… መልሱ “አያደርግም” ነው፡፡ የነቢዩንና የተከታዮቻቸውን የህይወት ታሪክ በወጉ ከፈተሽን ነገሩን በቀላሉ መረዳት እንችላለን፡፡ እስቲ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንውሰድ፡፡

·        ነቢዩ በዘመናቸው ለነበሩት ነገሥታት ደብዳቤ መጻፍ አስፈለጋቸው፡፡ አንዱ ባልደረባቸው “ደብዳቤው ከርስዎ የተላከ መሆኑን የሚያረጋግጥ ማኅተም ያስፈልግዎታል፤ ማኅተም ቢያስቀርጹ መልካም ይመስለኛል” አላቸው፡፡ ነቢዩ የማኅተም አስፈላጊነት ሲነገራቸው እምቢ አላሉም፡፡ ሃሳቡን ወዲያውኑ ተቀብለው አዲስ ማኅተም አስቀረጹ፡፡

·        ከሂጅራ በኋላ በስድስተኛው ዓመት የቁሬይሽ ተዋጊዎች በመዲና ከተማ ላይ ሶስተኛ ዙር ወረራ ሊፈጽሙ ተነሱ፡፡ ከቁሬይሾች ጋር በርካታ ማህበረሰቦች ማበራቸውም ተሰማ፡፡ ይህም ወሬ ለነቢዩ ደረሳቸው፡፡ ነቢዩም በጉዳዩ ላይ ከባልደረቦቻቸው ጋር መወያየት ጀመሩ፡፡ በውይይቱ ላይ ከነበሩት ባልደረቦቻቸው መካከል “ሳልማን አል-ፋርሲ” የሚባለው “በከተማችን ዙሪያ ምሽግ ብንቆፍር ጠላቶታችንን በቀላሉ መመለስ እንችላለን” አላቸው፡፡ ሳልማን የፋርስ (ኢራን) ተወላጅ ነው፡፡ በሀገሩ ሲደረግ ያየውን ነው ለነቢዩ የነገራቸው፡፡ እስከዚያ ጊዜ ድረስ “ምሽግ” በዐረቦች ዘንድ አይታወቅም ነበር፡፡

ነቢዩ ከሳልማን በሰሙት ምሽግ የመቆፈር ብልሃት ተገረሙ፡፡ በተግባር ላይ ሊያውሉትም ተነሱ፡፡ የመዲና ከተማን ከዳር እስከ ዳር በምሽግ ቁፋሮ አጠሯት፡፡ የመካ ቁረይሾች እየፎከሩ ወደ መዲና ሲመጡ ምሽጉ ገደባቸው፡፡ በፈረስና በእግር እየዘለሉ ምሽጉን ለማለፍ ቢሞክሩም ምንም አልተሳካላቸውም፡፡ ይህ ሁኔታ ሌሊቱን ከጣለው ከባድ ዝናብ ጋር ተዳምሮ በጣም አስፈራቸው፡፡ በመሆኑም እቃቸውን እንኳ በወጉ ሳይሰበስቡ ወደመጡበት ፈረጠጡ፡፡ ነቢዩ አንድም ጦር ሳይሰብቁ በእጥፍ የሚበልጣቸውን የጠላት ሃይል ከሳልማን አል-ፋርሲ በሰሙት ዘዴ አባረሩት፡፡

·        በዚያ ዘመን በርካታ መልዕክተኞች ወደ ነቢዩ ዘንድ ይመጡ ነበር፡፡ ታዲያ አንዱ የነቢዩ ባልደረባ “ንጉሦችና የጦር መሪዎች የውጪ መልዕክተኞችን በሚቀበሉበት ጊዜ የአዘቦት ልብሳቸውን አይለብሱም፤ ለየት ያለ ልብስ ለብሰው በርሱ ላይ ካባ ይደርባሉ” አላቸው፡፡ ነቢዩም ምክሩን ተቀብለው በተግባር ላይ አውለውታል፡፡

·        ነቢዩ አይጽፉም፤ አያነቡምም፡፡ ደብዳቤም ሆነ ሌላ ጽሑፍ የሚጽፉላቸው ተከታዮቻቸው ናቸው፡፡ ከጸሐፊዎቻቸው መካከል እጅግ በጣም የተከበረው ዘይድ ኢብን ሣቢት የሚባለው ወጣት ነው፡፡ ነቢዩ የላኳቸው ደብዳቤዎች በአብዛኛው በርሱ እጅ ነበር የተጻፉት፡፡

ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) በደብዳቤ የሚገናኟቸው የማህበረሰብ መሪዎችና ነገሥታት በሙሉ ዐረብኛን ማንበብ የሚችሉ አልነበሩም፡፡ ዐረብኛን የሚያነቡት በዐረቢያ ልሳነ-ምድር (Arabian Peninsula) እና በዙሪያው ባሉት መሬት ላይ የነገሡ መሪዎች ብቻ ነበሩ፡፡ በመሆኑም ነቢዩ ከዐረብኛ በተጨማሪ በሌሎች ቋንቋዎችም ደብዳቤዎችን መጻፍ እንዳለባቸው ተገነዘቡ፡፡ ዘይድ ኢብን ሣቢትንም በዘመኑ ሰፊ ተናጋሪ የነበራቸውን የእብራይስጥ (Hebrew) እና የአረማይስጥ (Aramaic/ Syriac) አጻጻፍ እንዲያጠና በመዲና ይኖሩ ከነበሩት አይሁዶችና ክርስቲያኖች ዘንድ ላኩት፡፡ ዘይድም ሁለቱንም አጻጻፎች በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጥናት የጸሐፊነቱን ስራ በሶሥት ቋንቋዎች ቀጥሎበታል፡፡

·        ነቢዩ ለዕውቀት የነበራቸው ከበሬታ ሲወሳ በዓለም ከሚኖሩት ሙስሊሞች ግማሽ ያህሉ የሚያውቁት አንድ ሐዲስ አለ፡፡ ሐዲሱ እንዲህ ይላል፡፡

“ዕውቀትን ቻይና ድረስ እንኳ ቢሆን ሄዳችሁ ፈልጉት”

ከላይ ከተገለጹት ታሪኮች እንደምትረዱት ነቢዩ ጠቃሚ የሆነ ዕውቀትን ያበረታቱ ነበር፡፡ “የተቀላጠፈ አሰራር መጠቀም ሀገርን ያጠፋል” በማለት በተከታዮቻቸው ላይ በሩን አልዘጉም፡፡ የርሳቸው ተከታዮችስ?… ባልደረቦቻቸውም ቢሆኑ በዘመናዊነት ላይ በነበራቸው እይታ የነቢዩን ፈለግ ተከትለዋል፡፡ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንጥቀስ፡፡

·        ኸሊፋ ዑመር ቢን ኸጣብ (ረ.ዐ) ከነቢዩ የቅርብ ረዳቶች አንደኛው ነበሩ፡፡ ከነቢዩ ህልፈት በኋላ የሙስሊሙን ኸሊፋዊ መንግሥት ለአስር ዓመታት መርተዋል፡፡ የነቢዩን ሐዲሶችን ጨምሮ በርካታ ታሪኮችን መመዝገብ የተጀመረው በርሳቸው ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ታሪክ ሲመዘገብ የዘመን መቁጠሪያ መጠቀም የግድ ይላል፡፡ ይሁንና በዚያ ዘመን ራሱን የቻለ የቀን መቁጠሪያ በዐረቢያ ምድር አይታወቅም ነበረ፡፡ በመሆኑም ዑመር ነቢዩ ከመካ ወደ መዲና ያደረጉት ስደት (ሂጅራ) እንደ መነሻ ሆኖ እንዲያገለግል ውሳኔ አስተላለፉ፡፡ ይህም ተግባራዊ ሆኖ እስከ አሁኑ ዘመን ድረስ እየተሰራበት ይገኛል፡፡

·        አምስተኛው ኸሊፋ ሙአዊያ ኢብን አቡ-ሱፍያን (ረ.ዐ) ደግሞ በተማከለ አሰራር ደብዳቤዎችን ከግለሰቦች ተቀብሎ የሚያከፋፍል ተቋም በመመስረት በዓለም ታሪክ አዲስ አሰራር አስተዋውቀል፡፡ ዛሬ “ፖስታ ቤት” የሚባለውን ተቋም የፈጠሩት ኸሊፋ ሙአዊያ ናቸው (ባለፈው ነሐሴ ወር ይህንን ጉዳይ በጻፍኩበት ወቅት በርካታ ሰዎች የግኝቱ ባለቤት ሙአዊያ መሆናቸውን እንደማያውቁት ተገንዝቤአለሁ፤ ሆኖም ነገሩ ሐቅ ነው፤ እውነትነቱን ለማረጋገጥ ካሻችሁ በመጽሐፍ፣ በኢንተርኔትም ሆነ በሲዲ የተሰራጨው “ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ” ስለሙአዊያ የጻፈውን ታሪክ አንብቡት፡፡ በሁሉም ቦታ እንዲህ የሚል ነገር ተጽፎ ታገኛላችሁ፡፡

“Early Arabic sources credit two dīwāns in particular to Muʿāwiyah: the dīwān al-khatam, or chancellery, and the barīd, or postal service, both of which were obviously intended to improve communications within the empire”
የኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካን ጽሑፍ በኢንተርኔት ለማንበብ ካሻችሁ ይህንን ሊንክ ተጠቀሙ፡፡

·        በአሁኑ ወቅት የዓለም ህዝብ በሙሉ የሚጠቀምበት “የሂንዱ-ዐረብ” የቁጥር ዘዴ የመጨረሻ ቅርጹን ያገኘው በሙስሊሞች አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ለሂሳብ አቆጣጠር የሚያመቸው “የዜሮ ጽንሰ ሃሳብ” የተፈለሰፈው በ8ኛው ክፍለ ዘመን በባግዳድ ከተማ ነው፡፡

·        የሳይንስና የምርምር ዘርፍ ከፍተኛ እመርታ እንዲሳይ ያደረጉትን አል-ጀብራ እና አልጎሪዝም የተሰኙ የሂሳብ ስልቶችን የፈጠረው ሙሐመድ ኢብን ሙሳ አል-ኸዋሪዝሚ የተባለ ሙስሊም ሳይንቲስት ነው (ዜሮንም የፈጠረው አል-ኸዋሪዝሚ ነው)፡፡

·        ሌላም ብዙ ብዙ መዘርዘር ይቻላል፡፡

ከነዚህ ምሳሌዎች ለመረዳት እንደሚቻለው የጥንቱ ሙስሊሞች በአዳዲስ ፈጠራዎች ከመጠቀም አልፈው ለራሳቸውም ልዩ ልዩ ፈጠራዎችን አስተዋውቀዋል፡፡ በአዳዲስ ፈጠራዎች መጠቀም “ውግዝ” ቢሆን ኖሮ ነቢዩና ባልደረቦቻቸው “እርም፤ ነው አትጠጉት” በማለት ክልከላ ያስቀምጡበት ነበር፡፡ ስለዚህ ዘመን ባስገኘልን ትሩፋት ከመጠቀም ወደኋላ ማለት የለብንም፡፡

ይሁንና ይህ በፈጠራዎች የመጠቀም ጉዳይ ሲነሳ አንድ ነገር መታወቅ አለበት፡፡ ይኸውም በጥቅም ላይ የሚውለው አዲስ ፈጠራና አሰራር የሰዎችን ኑሮ በማቃለል ረገድ አስፈላጊነቱ የሁሉም ተጠቃሚዎች ምስክርነት ሊኖረው የተገባ መሆኑ ነው፡፡ እስልምና ከጉዳት በስተቀር አንዳች ጥቅም የሌለውን ፈጠራ ይከለክላል፡፡

 በሌላ በኩል ደግሞ በፈጠራና በዘመናዊነት ስም አላህ እርም ያደረጋቸውን ድርጊቶች መፍቀድ አይቻልም፡፡ ለምሳሌ ማንኛውም የእስልምና ሙፍቲ “አስካሪ መጠጥ ለጤና ይጠቅማችኋል፣ ድንበር ሳታልፉ ጠጡ” በማለት ውሳኔ መስጠት አይችልም፡፡ ቁማርን ህጋዊ ማድረግም በፍጹም አይቻልም፡፡ በሰብዓዊ መብት ስም ግብረ-ሰዶምን ህጋዊ ማድረግም ተቀባይነት የለውም፡፡ እነዚህ ድርጊቶች የሰዎችን ኑሮ ከማቃወስ በስተቀር አንዳች ጠቀሜታ የላቸውም፡፡

ነቢዩ በዘመናዊ እውቀት መጠቀምን ከልክለዋል የሚል የተቀዣበረ ወሬ የሚነዙት ነቢዩን የማያውቁት ጠላቶቻቸው ብቻ አይደሉም፡፡ “የነቢዩን ትክክለኛ ትምህርት የምንከተለው እኛ ብቻ ነን” ማለት የሚቃጣቸውና ሰዎችን “አዛ” ማድረግ ልማዳቸው የሆነ ከሙስሊሙ ዓለም የበቀሉ አንዳንድ ጽንፈኛ አንጃዎችም ጭምር ናቸው፡፡ ለምሳሌ የ“ጣሊባን” አንጃ አፍጋኒስታንን በሚያስተዳድርበት ጊዜ “በእስልምና የተከለከሉ ናቸው” በሚል በርካታ የቴክኖሎጂ ትሩፋቶችን እርም አድርጎ ነበር፡፡ ይሁንና ነቢዩ እንዲህ ዓይነት ጽንፈኝነትን አላስተማሩም፡፡ አላህ ነቢዩን የላከለው ለራሕመት (እዝነት) ነው እንጂ ጽንፍ በወጣ አስተምህሮ ሰዎችን እግር ተወርች ቀፍድደው ለሰቀቀን ኑሮ እንዲዳርጓቸው በሚል አይደለም፡፡ ነቢዩም ተከታዮቻቸውን ሲያስተምሩ “አግራሩ፤ አታክርሩ” (“የሲሩ፤ ወላ ቱዐሲሩ”) ነበር ያሉት፡፡ በመሆኑም የነዚህን ጽንፈኞች አድራጎት በማየት የነቢዩን አስተምህሮ በተዛነፈ ሁኔታ መረዳት ተገቢ አይደለም፡፡

የአላህ ሶላትና ሰላም በነቢዩ ላይ ይስፈን (ሰልላሁ ዐለይሂ ወሰለም)

——

አፈንዲ ሙተቂ

ጥር 9/2015

—–

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

—–

ከዚህ በፊት “እስልምና ጂሃድ እና ሰሞነኛው የኢራቅ ሚሊሻ” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ጽሑፍ የእስልምና ሃይማኖት በጽንፈኝነት ላይ ያለውን አቋም በሰፊው ገልጫለሁ (ጽሑፉ የኔ ብሎግ ላይ ስላለ ከዚያ ማንበብ ይቻላል)፡፡ በጽሑፉ ለማስረዳት እንደሞከርኩት በእስልምና የሚያምነው የዓለም ህዝብ ጽንፈኝነትና ጽንፈኞችን በጣም ያወግዛል፡፡ ከብዙሃን ጋር የማይጣጣሙት ጥቂት ጽንፈኞች እስልምናንም ሆነ ሙስሊሞችን አይወክሉትም፡፡

  ይሁንና ምዕራባዊያንና ሚዲያዎቻቸው ጽንፈኝነትን ለአንዱ ሃይማኖት በጅምላ ያሸከሙ ነው የሚመስሉት፡፡ ታላቋ ሶቪየት ህብረት ከፈራረሰች ወዲህ ከሚዲያ ኢንዱስትሪው ወሬ ማሟሟቂያዎች እና ከተንታኞቻቸው የአስተሳሰብ ምጡቅነት ማሳያ ዋነኛ አርዕስተ ጉዳዮች አንዱ ስለ“እስልምና አክራሪነት” መፍተልና መተርተር ሆኗል፡፡ እንግዲህ የ“እስልምና አክራሪነት” የሚል ርዕስ ከመጠቀም ጀምሮ የዓለም ማህበረሰቦች አትኩሮት በርሱ ላይ ብቻ እንዲሆን መጣሩ ከጀርባው ሌላ ነገር ያለ ነው የሚመስለው፡፡

“ጽንፈኝነት”ም ሆነ “አክራሪነት” በሀይማኖት ያልተገደቡ ናቸው፡፡ ጽንፈኛ ቡድኖች ከየትኛውም ሀይማኖት ሊመነጩ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ በጥንት ዘመን “Masada” የተሰኘ የአይሁዳዊያን ጽንፈኛ ቡድን ነበር፡፡ ዛሬም በእስራኤል ውስጥ በመቶ የሚቆጠሩ እጅግ ጽንፈኛ ቡድኖች አሉ፡፡ በ7ኛው ክፍለ ዘመን ደግሞ “ኸዋሪጃ” የሚባሉት ጽንፈኞች ከሙስሊሙ ዓለም ተነስተዋል፡፡ በዘመናችንም አል-ሸባብ፣ አል-ቃኢዳ፣ ቦኮ ሀራም የመሳሰሉት ተፈጥረዋል፡፡ ከክርስትናው ዓለምም በ“መስቀል ጦርነት” የሚያምኑ ጽንፈኛ ቡድኖች በተለያዩ ዘመናት ተነስተዋል፡፡ በዘመናችን በሰሜን ኡጋንዳ ጫካዎች ውስጥ መሽጎ ልዩ ልዩ ሰቆቃዎችን የሚፈጽመው Lords Resistance Army የተባለው ሚሊሺያ “ኡጋንዳን በወንጌልና በአስርቱ ትዕዛዛት እመራታለሁ” እያለ የሚለፍፍ ጽንፈኛ ቡድን ነው፡፡ ከሶስት ዓመታት በፊት ከሰማኒያ የሚበልጡ ንጹሃንን የጨፈጨፈው የኖርዌይ ጽንፈኛ ግለሰብም በሃይማኖቱ ክርስቲያን ነው፡፡ በጃፓን ሜትሮ (የምድር ውስጥ ባቡር) ውስጥ የመርዝ ጋዝ በመርጨት ንጹሃንን የፈጀው የኡም-ሺኖሮኪዮ ሀይማኖታዊ ቡድን “የፈጣሪን ትዕዛዝ እተገብራለሁ” የሚል ጽንፈኛ ነው፡፡ በሀይማኖት የማያምኑ (ማቴሪያሊስቶች፣ ኮሚንስቶች ወዘተ…) ጽንፈኛ ቡድኖችም በልዩ ልዩ ዘመናት ተነስተዋል፡፡የሚዲያው አካሄድ ግን ይህንን ሐቅ የተከተለ አይደለም፡፡ በአያያዙ ወደ አንዱ አቅጣጫ የተንጋደደ ነው፡፡ ይህ አድልኦ በግልጽ እየታየ ጽንፈኝነት ይጠፋል ማለት ዘበት ነው፡፡

ሌላኛው ደግሞ ሚዲያው ወሬ በማጋጋል ረገድ የሚጫወተው ሚና ነው፡፡ በልዩ ልዩ እምነቶችና ማህረበሰቦች ዘንድ እንደ ጸያፍ የሚታዩ ድርጊቶች በአንድ የዓለም ክፍል ሲፈጸሙ ሚዲያው ሽፋን የሚሰጣቸው አስቀድሞ በተቀመጠለት እቅድ ሳይሆን እንደማይቀር እገምታለሁ፡፡ እነዚህ ድርጊቶች መከሰታቸው እንዲታወቁ ሚዲያው ቶሎ ብሎ ወሬ ማራገብ ይጀምራል፡፡ ከሰዓታት ወይንም ከአንድ ቀን በኋላ ድርጊቱ ቁጣን ቀሰቀሰ ተብሎ ሌላ ወሬ ይራገባል፡፡ በሶስተኛው ቀን በቁጣው የተነሳሱ ጽንፈኞች ሰላማዊ ሰዎችን ገደሉ ተብሎ ይራገባል፡፡ በዚህ እርግብግቦሽ መሃከል ሌላ ቁጣ ይቀሰቀሳል፡፡ ሚዲያው እርሱንም ያራግባል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ ይቀጥላል፡፡

እንደዚህ ዓይነቶቹ ድርጊቶች ቀድሞውኑ የሚዲያ ሽፋን እንዲኖራቸው ባይደረግ ኖሮ የሚጠፋ ህይወትም ሆነ የሚበላሽ ንብረት ባልኖረ ነበረ፡፡ ነገር ግን ሚዲያው በሰዎች ስነ-ልቦና እየተጫወተ ድብቅ ተልዕኮውን ይፈጽማል፡፡ እግረ መንገዱንም ለራሱ ከፍተኛ ገቢ ይሸቅላል፡፡

 ይህንን ስጽፍ “International Qur’an Burning” ብሎ ዓለምን ለመጥበጥ የሞከረው ፓስተር ትዝ አለኝ፡፡ ሰውዬው የሚመራው Church መቶ አባላት እንኳ አልነበሩትም፡፡ ነገር ግን ሰውዬው እንዲያ አደርጋለሁ ብሎ ሲነሳ ሚዲያው ወሬውን እየተቀባበለ በዓለም ዙሪያ አዳረሰው፡፡ ዓለምም ለአስራ አምስት ቀን ተንጫጫ፡፡ ከዚያ ሰውዬው እቅዱን ሰረዘው ተብሎ ተነገረን፡፡ ሰውዬው የሰጠው ምክንያትም “በኒውዮርክ መንትያ ህንጻዎች ፊት ለፊት የሚሰራው መስጊድ ከተከለከለ እኔም እቅዴን እተወዋለሁ” የሚል ነበር፡፡እንግዲህ የሰውዬው ፍላጎት ቁርኣኑን ማቃጠል ሳይሆን የመስጊዱ ግንባታ እንዲቆም ማድረግ ነበር ማለት ነው፡፡ ሚዲያው ወሬውን እያጋነነው በዓለም ዙሪያ አዳረሰውና የልቡ እንዲደርስለት አደረገ፡፡ የሚዲያው ጫጫታ በጥርጣሬ መታየት አለበት የምለው ይህንን የመሳሰሉ በርካታ ታሪኮች ስላሉ ነው፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ መታየት ያለበት ሌላው ነገር በዲሞክራሲ ስም የሌሎች እምነት ተከታዮችን ስነ-ልቦና የሚጎዱ አድራጎቶችን መፈጸሙ ነው፡፡ እነዚህ ተንኳሾች ሌሎች እንዲነኩባቸው የማይፈቅዷቸውን ነቢያት፣ ቅዱሳት እና መጻሕፍት በወረደ አኳሃን ይነካካሉ፡፡ የእምነቱ ተከታዮች ስለመብታቸው ሲጮኹ ደግሞ “በእገሌም እኮ ይቀለዳል” የሚል ምላሽ ይሰጣቸዋል፡፡ ይሁንና እነዚህ ቧልተኞች የማይደፍሯቸው ጥቂት ክፍሎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ““Holocaust is a lie” ከተባለ በህግ ይጠየቃሉ፡፡ በነቢዩ ሙሐመድ እና በእየሱስ ክርስቶስ ሲቀልዱ ግን የዲሞክራሲ መብታቸው ነው ይባላል፡፡ “እንስሳት እኩል ናቸው፤ አንዳንዶቹ ግን በጣም እኩል ናቸው” የሚለው የጆርጅ ኦርዌል አባባል በሁሉም ቦታ ይሰራል ማለት ነው፡፡ ይሁንና እንዲህ ዐይነቱ ዓይን ያወጣ አድልኦ እየተደረገ ጽንፈኝነት በጭራሽ አይጠፋም፡፡ ስለዚህ ጽንፈኝነትን ለማጥፋት ከተፈለገ መከባበርን እንደ መርህ መያዝ ይገባል፡

*****

  ጽንፈኝነት ምንጊዜም ቢሆን አደገኛ ነው፡፡ የዓለምን ሰላምና የህዝቦችን አብሮ የመኖር ተስፋ ይገድላል፡፡ ስለዚህ የዓለም ህዝቦች ሁሉ በጋራ ሊታገሉት ይገባል፡፡ በተለይም በየሀገሩ ያሉ የየሃይማኖት ምሁራን እርስ በራሳቸው ሃሳቦችን የሚለዋወጡባቸው የ“Inter-faith” ፎረሞች ሊጠናከሩ ይገባል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ሚዲያው አድሎአዊነቱንና ድብቅ ተልዕኮ ፈጻሚነቱን ትቶ ሁሉንም ህዝቦች እኩል የማየትን ልማድ ማምጣት አለበት፡፡ እኛ አድማጮችና ተመልካቾችም ሚዲያው የሚዘበዝበውን ወሬ እንዳለ ከመቀበላችን በፊት ነገሮችን ከሁሉም አቅጣጫ መመልከት አለብን እላለሁ፡፡

አፈንዲ ሙተቂ

ጥር 2/2007 ተጻፈ፡፡

——


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
ቅዱስ ቁርኣን በአማርኛ እንዲተረጎም ትዕዛዝ ያስተላለፉት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ነበሩ፡፡ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ትዕዛዙን የሰጡት ወዳጆቻቸው ከነበሩት የግብጹ መሪ ጀማል አብዱናሲር እና የሳዑዲ ዐረቢያው ንጉሥ ፈይሰል ቢን ዐብዱል አዚዝ “ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች እምነታቸውን በራሳቸው ቋንቋ እንዲማሩ ሊደረግ ይገባል” የሚል ጫና ስለመጣባቸው እንጂ በራሳቸው ተነሳሽነት አልነበረም፡፡ ቢሆንም ንጉሡ እንዲህ ዓይነት ስራዎች መፈጸማቸውን ቀርቶ መታሰባቸውን እንኳ እንደ ድፍረት ይቆጥሩ የነበሩትን የወግ አጥባቂ መኳንንትና መሳፍንትን ተቃውሞ ሳይፈሩ ስራው እንዲጀመር በመወሰናቸው ሊመሰገኑ ይገባል፡፡
ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ትእዛዙን ያስተላለፉት ሐምሌ 18/1958 በተጻፈ ደብዳቤ ነበር፡፡ የንጉሡን ደብዳቤ በመንተራሰስ ስራው እንዲጀመር ያደረጉት ደግሞ በወቅቱ የትምህርት ሚኒስትር የነበሩት ዶ/ር ምናሴ ሃይሌ ናቸው፡፡ ዶ/ር ምናሴ በተርጓሚነት የመረጡት ከአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ ተመርቀው በማስታወቂያ ሚኒስቴር ስር የሚታተመው የ“አል-ዐለም” ጋዜጣ ምክትል ዋና አዘጋጅ በመሆን ይሰሩ የነበሩትን ሐጂ በሺር ዳውድን ነው (ሐጂ በሺር እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ የተገነባው ትልቅ መስጂድ ኢማም እንደነበሩ አውቃለሁ፤ በሚዲያም አንድ ሁለቴ አይቼአቸኋለሁ፤ አሁን በህይወት ይኖሩ ይሆን?… እስቲ መረጃ ካላችሁ አቀብሉን)፡፡
ሐጂ በሽር ከዶ/ር ምናሴ የተሰጣቸውን አመራር በግርድፉ አልተቀበሉትም፡፡ “ቁርኣንን መተርጎም ሌሎች መጽሐፍትን እንደ መተርጎም ተደርጎ ሊታይ አይገባም፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ኮሚቴ ተዋቅሮ ኮሚቴው በሚሰጠው መመሪያ መሰረት ነው መሰራት ያለበት” የሚል ምላሽ ነበር የሰጡት፡፡ አባባላቸው ተቀባይነት በማግኘቱም የቁርኣን ትርጉም ኮሚቴው ተዋቀረ፡፡ ከሀገር አቀፉ ኮሚቴ አባላት መካከል እንደርሳቸው የአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ ምሩቅ የነበሩት ሼኽ ዓብዱል ከሪም ኑርሑሴን እና ሙሴ ሰሊም ቡሽቅራ ይጠቀሳሉ፡፡
  ኮሚቴው የትርጉሙን ስራ በብቃት ማከናወን የሚችሉ ዓሊሞችን ማፈላለግ ጀመረ፡፡ በወቅቱ ትልቁ ችግር የነበረው በእስላማዊ እውቀትም ሆነ በዓለማዊ ትምህርቱ ብቁ የሆነ ዓሊም ማግኘት ነበር፡፡ በተለይም አማርኛ ቋንቋን አስተካክሎ ከመጻፍ ጀምሮ የቋንቋውን የሰዋስው እና የስነ-ልሳን ህግጋትን ጠንቅቆ የሚያውቅ ዓሊም ማግኘቱ አስፈላጊ ነበር፡፡ ብዙዎቹ ዓሊሞቻችን የመጀመሪያውን መስፈርት ቢያሟሉም የኋለኛው ይጎድላቸው ነበር፡፡ ሆኖም ኮሚቴው በሓጂ በሺር ዳውድ ጠቋሚነት ሁለት ሰዎችን አገኘ፡፡ እነርሱም በጊዜው በደሴ ከተማ በሚገኘው የወይዘሮ ስሒን ትምህርት ቤት የሚያስተምሩት ሓጂ ሙሐመድ ሣኒ ሐቢብ እና የሸሪዓ ፍርድ ቤት ዳኛ የነበሩት ሼኽ ሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅ ነበሩ፡፡ በዚህ መሰረት ሁለቱ ዓሊሞች ዋና ተርጓሚ ሆነው ስራቸውን ጀመሩ፡፡ ሓጂ በሺር ዳውድ እና ሼኽ ዐብዱል ከሪም ኑርሑሴን ደግሞ ተባባሪ ኤዲተሮች ሆነው እንዲሰሩ ተመደቡ፡፡
ተርጓሚዎቹ ከኤዲተሮቹ ጋር በቅርበት እየሰሩ በአስራ አምስት ወራት ውስጥ ስራቸውን አጠናቀቁት፡፡ ሆኖም ከየክፍለ ሀገሩ የተመረጡ ዑለማ የትርጉሙን ረቂቅ አንብበው የእርማትና የማሻሻያ ሓሳቦችን እንዲሰጡበት ያስፈልጋል የሚል ሃሳብ ተሰነዘረ፡፡ በዚሁ መሰረት የሚከተሉት ታላላቅ ዑለማ ወደ ኮሚቴው ቀርበው ረቂቅ ስራውን በማንበብ ሃሳባቸውን እንዲሰጡበት ተደረገ፡፡
ሼኽ ቡሽረል ከሪም ሙስጠፋ (ከወሎ)
ሓጂ ዩሱፍ ዐብዱራሕማን ገራድ (ከሀረርጌ)
ቃዲ ሙሐመድ ዐብዱራሕማን (ከትግራይ)
ሓጂ አሕመድ ዳለቲ (ከሸዋ)
ሓጂ መንዛረሁ ከቢር ሑሴን (ከአርሲ)
በመጨረሻም ተርጓሚዎቹ ከአምስቱ ዑለማዎች የተሰጡትን አስተያየቶችና ሌሎች የማሻሻያ ሃሳቦችን በመቀበል ረቂቁን አርመው አዘጋጁ፡፡ አሁን በእጃችን ላይ የሚገኘው የቅዱስ ቁርኣን የአማርኛ ትርጉምም በ1961 የመጀመሪያ ወራት ውስጥ ለህትመት በቃ፡፡
—–
ቅዱስ ቁርኣን በአማርኛ የተተረጎመበት ሂደት ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡ ይሁንና አንዳንድ ጸሐፊዎችና ደራሲዎች ይህንን ታሪክ እንዳሻቸው ሲጽፉት ተመልክተናል፡፡ ለምሳሌ ፕሮፌሰር ሃጋይ ኤልሪችን የመሳሰሉ ፀሐፍት የትርጉም ስራው ባለቤትና መሪ አድርገው የሚጠቅሱት ተርጓሚዎቹ ረቂቁን ከጨረሱ በኋላ በኮሚቴው ጋባዥነት ሃሳባቸውን ከሰጡት አምስት ዑለማ መካከል አንዱ የነበሩትን  ሓጂ ዩሱፍ ዐብዱራሕማንን ነው፡፡ ፕሮፌሰር ኤልሪች ዋነኞቹ ተርጓሚዎቹ ሓጂ ሙሐመድ ሣኒ እና ሼኽ ሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅ መሆናቸውን አጥተውት አይደለም ይህንን የሚያደርጉት፡፡ እርሳቸው ዘወትር “አሕባሽ እና ወሃቢያ” እያሉ በሚያቀርቧቸው መጣጥፎች  ውስጥ ከፍተኛ የአትኩሮት ማዕከል አድርገው የቀረጿቸውን ሓጂ ዩሱፍ ዐብዱራሕማንን ለማጥቆር ሲሉ ነው እንዲህ ዓይነት ታሪክ የሚጽፉት፡፡ የሚገርመው ደግሞ ሌሎች ምሁራን ይህንኑ የሃጋይ ኤልሪችን ትረካ እንደ ወረደ ተቀብለው ማስተጋባታቸው ነው፡፡ ለምሳሌ ፕሮፌሰር ፓትሪክ ዴስፕላት የሚባሉት ጀርመናዊ ምሁር በአንድ ጽሑፋቸው እንዲህ ይሉናል፡፡
“Hadj Yusuf became closer to the Ethiopian government and supervised the first official translation of the Quran into Amharic, published in 1961”.
(Patrick Desplat, The Articulation of Religious Identities and their Boundaries in Ethiopia: A Case Study on Harar, Journal of Religions in Africa, Lieden, 2005, pp 497)
  እርግጥ ሓጂ ዩሱፍ ቅዱስ ቁርኣንን የመተርጎም ብቃት ያላቸው ዓሊም ነበሩ፡፡ ከእዉቁ የመዲና ዩኒቨርሲቲ የተመረቁ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ከመሆናቸውም ባሻገር የአማርኛ ቋንቋ እውቀታቸውም ከፍተኛ ነበረ፡፡ በህይወት ሳሉም ለኢትዮጵያን ሙስሊሞች ብዙ ውለታዎችን ውለዋል (አንዳንዶቹን በቅርቡ እናያቸዋለን)፡፡ ፕሮፌሰር ሃጋይ ኤልሪች ይህንን የሐሰት ትረካ የፈጠሩት ግን መልካም ስራቸውን ለማውሳት አስበው ሳይሆን “ሓጂ ዩሱፍ የንጉሡ ቀኝ እጅ ነበሩ” የሚለውን የተቃዋሚዎቻቸውን ክስ ለማጠናከር በሚል ነው፡፡
ማንም ያሻውን ይበል፡፡ ቅዱስ ቁርኣን ወደ አማርኛ የተተረጎመበት ትክክለኛው ሂደት ከላይ የገለጽኩት ነው፡፡ በእኛ በኩል በትርጉም ስራው ላይ በተሳተፉት ዑለማዎቻችን መካከል አንዳች ልዩነት አናደርግም፡፡ ሁለቱ ተርጓሚዎች፤ ሁለቱ ኤዲተሮችና ከየክፍለ ሀገሩ የተመረጡት አምስቱ አራሚዎች በሙሉ ባለውለታዎቻችን በመሆናቸው ዘወትር እናስታውሳቸዋለን፡፡ አላህ የበጎ ስራቸውን ምንዳ በጀንነት ይክፈላቸው፡፡ አሚን!!

——
አፈንዲ ሙተቂ
ታሕሳስ 22/2007
ሀረር-ምሥራቅ ኢትዮጵያ

——-
ምንጮች
1.      ቅዱስ ቁርኣን፡ የአማርኛ ትርጉም በሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅ እና ሐጂ ሙሐመድ ሣኒ ሐቢብ፣ 1961፣ አዲስ አበባ
2.     “ቢላል መጽሔት”፡ ቅጽ 1፡ ቁጥር 9፡ ግንቦት 1985
3.     ቢላል መጽሔት፡ ቅጽ 1፡ ቁጥር 11፡ ሐምሌ 1985
4.      Patrick Desplat, The Articulation of Religious Identities and their Boundaries in Ethiopia: A Case Study on Harar, Journal of Religions in Africa, Lieden, 2005
5.     Haggai Elrich: Islam and Christianity in the Horn of Africa, Lynne Rienner Publishers, Inc, Boulder, 2010
6.    Haggai Elrich: Saudi Arabia and Ethiopia, 2003, London
——
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links


 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

——

 

——
አንድን መጽሐፍ ከአንድ ጊዜ በላይ የማንበብ ልማድ የለኝም፡፡ አንዳንድ መጻሕፍትን ግን ሃያ፣ ሰላሣ እና አርባ ጊዜ ያህል እየደጋገምኩ አንብቤአቸዋለሁ፡፡ ከነዚያ መጻሕፍትም አንዱ “እስልምና እና የታላቁ ነቢይ የሙሐመድ ታሪክ” የሚል ርዕስ አለው፡፡ ደራሲው ደግሞ በፎቶግራፉ ላይ የምታዩዋቸው ሃጂ ሙሐመድ ሣኒ ሐቢብ ናቸው፡፡
የሓጂ ሙሐመድ ሣኒን መጽሐፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነበብኩት በታተመበት ዓመት ውስጥ (በ1980) ነው፡፡ መጽሐፉ ከአዕምሮ ሊጠፋ ያልቻለበት አንዱ ምክንያት በልጅነቴ ያነበብኩት መሆኑ ይመስለኛል፡፡ ከዚያ ወዲህም ለበርካታ ጊዜያት አንብቤዋለሁ፡፡ በሀገራችን ውስጥ እስከ 1980ዎቹ አጋማሽ ድረስ እስልምናን በተመለከተ እንደ መጣቀሻ ሆነው ይወሰዱ የነበሩት ከአማርኛው የቅዱስ ቁርኣን በተጨማሪ ይህ የሓጂ ሣኒ መጽሐፍ እና በአቶ አብዱልዋሲዕ መንዲዳ የተጻፈው “መልዕክተ እስላም” ነበሩ (በዘመነ ኃይለ ሥላሤ “ማዕሙን ማሕዲ” የሚባሉ ሰው “ተውሂድና ፊቅህ” የተባለ መጽሐፍ አሳትመው ነበር፤ ሐጂ ሣኒም “የሰላት መማሪያ” የሚባል መጽሐፍ በ1960ዎቹ መጨረሻ ላይ አሳትመዋል፤ ይሁንና እነዚህ ሁለት መጻሕፍት መኖራቸውን የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው)፡፡
  እንግዲህ ዛሬ በመጻሕፍት መሸጫ ሱቁና በየሼልፉ ለሞሉት እስላማዊ የአማርኛ መጻሕፍት ፋና ወጊ የሆኑት እነዚያ ሁለት መጻሕፍት ነበሩ፡፡ እኛንም በልጅነት ዕድሜአችን ኮትኩተው በማሳደግ የላቀ ሚና ነበራቸው፡፡
——-
ሐጂ ሙሐመድ ሣኒ ከዚያች መጽሐፍ በፊት (በ1963) ከሼኽ ሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅ ጋር በመሆን ቅዱስ ቁርኣንን ወደ አማርኛ ተርጉመዋል፡፡ ያ የቁርኣን ትርጉም በዚህ ዘመን እየወጡ ካሉት ትርጉሞች በብዙ መልኩ ይለያል፡፡ አንድ ሰው ከቁርኣን ፍቺ ከሚያገኘው መልዕክት በተጨማሪ የዐረብኛ ሰዋስውን ባህሪ ለማወቅ ካሻው ከዚያ የትርጉም ስራ ብዙ ቁም ነገሮችን ይማራል፡፡  ለምሳሌ እኔ አፈንዲ በዐረብኛ የሚታወቁትንና በአማርኛ ውስጥ የሌሉትን የአገናዛቢ አጸፋ ተውላጠ ስሞችን አጠቃቀም ለመጀመሪያ ጊዜ ያወቅኩት ከዚያ የቁርኣን ትርጉም መሆኑን እመሰክራለሁ፡፡ ለዚህም አንድ አብነት ብቻ ልስጣችሁ፡፡ ዐረብኛው “ዛሊከ” ሲል “ይህ” ማለት ነው፤ ይህንኑ ተውላጠ ስም ወደ ብዙ ቁጥር ስንቀይረው “ዛሊኩም” ይሆናል፤ ይህም በአማርኛ ሲፈታ “ይሃችሁ” እንደማለት ነው፤ በትርጉም ስራው ውስጥም ይህንኑ የተውላጠ ስም አጠቃቀም በደንብ ታያላችሁ)፡፡
  በሌላ በኩል በአማርኛ “አጎት” ከተባለ የእናት ወይም የአባት ወንድም ማለት ነው፡፡ አክስት ከተባለ ደግሞ የእናት ወይም የአባት እህት ማለት ነው፡፡ በእንግሊዝኛም ሁለቱንም አጎቶች uncle እንላቸዋለን፡፡ ሁለቱን አክስቶች aunt ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ በዐረብኛ፤ በኦሮምኛ፣ በሀረሪ እና በሶማሊኛ ቋንቋዎች ግን ሁለቱ አጎቶች እና ሁለቱ አክስቶች በተለያዩ ስሞች ነው የሚጠሩት፡፡ በዐረብኛ የእናት ወንድም የሆነው አጎት “ኻል” ነው የሚባለው፡፡ የእናት እህት ደግሞ “ኻላህ” ትባላለች፡፡ የአባት ወንድም “ዓም” የሚባል ሲሆን የአባት እህት “ዓምማህ” ትባላለች፡፡ እንግዲህ ቁርኣን በዐረብኛ የወረደ እንደመሆኑ ሁለቱን አጎቶች በዐረብኛው ስልት “ኻል” እና “ዓም” እያለ ነው የሚጠራቸው፡፡ ሁለቱ ሰዎች በአማርኛ ቋንቋ በአንድ ዘርፍ “አጎት” ተብለው ከተጠሩ የቁርኣን ፍቺ የተዛባ ሊሆን ነው (ለምሳሌ “ኻል” እና “ዓም” እኩል የወራሽነት ድርሻ የላቸውም፤ በመሆኑም ሁለቱ ሰዎች “አጎት” ተብለው ከተጠሩ ይህንን ልዩነት ማስገንዘብ ከባድ ሊሆን ይችላል)፡፡
እነ ሓጂ ሣኒ ይህንን ክፍተት ለመሙላት “አሪፍ” ቀመር ነው የተጠቀሙት፡፡ ይህም በወሎ ከሚነገረው የደዌ ኦሮምኛ ዘዬ ተጨማሪ ቃላትን መደበር ነው፡፡ በዚህም መሰረት እነ ሓጂ ሣኒ ባሳተሙት የቁርኣን ፍቺ ውስጥ “አጎት” ማለት የአባት ወንድም ብቻ ነው፡፡ የእናት ወንድም ደግሞ “የሹማ” ተብሎ ነው የተጠራው (የደዌ ኦሮሞዎች ናቸው እንዲህ የሚሉት፤ ሌላው ኦሮሞ “ኤሱማ” ነው የሚለው)፡፡ የአባት እህት “አክስት” የተባለች ስትሆን የእናት እህት ደግሞ “የሹሜ” ተብላ ተሰይማለች፡፡ በዚህ ዓይነት ዘዴ የቁርኣኑን የዐረብኛ መልዕክት ያለምንም ችግር ወደ አማርኛው ለመመለስ ተችሏል፡፡
በቅዱስ ቁርኣኑ ፍቺ ውስጥ አጽንኦት የተሰጠው ሌላው ጉዳይ ደግሞ የድምጾችና የፊደላት ውክልና ነው፡፡ እንደሚታወቀው በዐረብኛና በግዕዝ ቋንቋዎች ውስጥ ያሉ በርካታ ድምጾችን በአማርኛ ውስጥ አናገኛቸውም፡፡ በአማርኛ “አ” እና “ዐ” እየተባለ ቢጻፍም በንባብ ደረጃ ምንም ልዩነት አናደርግባቸውም፡፡ በግዕዝና በትግርኛ ቋንቋዎች ግን ሁለቱ ፊደላት የተለያዩ ድምጾችን ነው የሚወክሉት፡፡ ዐረብኛም “የአንድ ፊደል ለአንድ ድምጽ” መርህን የሚከተል ቋንቋ በመሆኑ በጽሑፍ ጊዜ ጥንቃቄ ይደረጋል፡፡ እነ ሓጂ ሣኒ ቁርአኑን በአማርኛ ሲተረጉሙ በተለይ የተጸውኦ ስሞች በኦሪጂናሌው ድምጽ መጠራት እንዳለበት አምነዋል፡፡ በመሆኑም በትርጉም ስራው ውስጥ ያሉት የተጸውኦ ስሞች ይህንን መርህ በመከተል ነው የተጻፉት፡፡ ለምሳሌ በትርጉሙ ውስጥ “ያሕያ” እንጂ “ያህያ” የሚል ስም አታገኙም (“ሐ” ቀጭኑንና በጉረሮ የሚነገረውን የዐረብኛውን “ሐእ” ነው የሚወክለው፤ ሃሌታው “ሃ” ደግሞ “ዋው” ከተሠኘው የዐረብኛ ፊደል አጠገብ የሚገኘውን ወፍራሙን “ሀ” ነው የሚወክለው)፡፡  የመርየም ልጅም “ዒሳ” እንጂ “ኢሳ” ተብሎ አልተጠራም፡፡ “ዒስማኢል”፣ “ኢብራሂም”፣ “አዩብ”፣ “ኢስሓቅ”፣ “ያዕቁብ”፣ ወዘተ… አሁን በጻፍኩት መልኩ ነው የተጠሩት፡፡
 
  ከዚህ ሌላ እነ ሓጂ ሣኒ በጥንታዊው ዐረብኛ ያሉትን ቃላት ለመጥራት ሲሉ ከየገጠሩ የሰበሰቧቸው ጥንታዊ የአማርኛ ቃላት በጣም ያስድምማሉ፡፡ “ዘለበት”፣ “ቀንዘል”፣ “እንዛዝላ”፣ “ሰርክ”፣ “አጎበር” ወዘተ…. የመሳሰሉ ቃላትን ለመጀመሪያ ጊዜ ያወቅኩት ከዚሁ የቅዱስ ቁርኣን ትርጉም ነው፡፡
  አንዳንድ ሰዎች የነ ሐጂ ሣኒ የቁርኣን ትርጉም ይከብደናል ይላሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በመጽሐፉ መጀመሪያ ላይ ያለውን መቅድም ስለማያነቡት ይመስለኛል ፍቺው ከበደን የሚሉት፡፡ መቅድሙን በአትኩሮት ያነበበ ሰው ምንም ግራ የሚገባው አይመስለኝም፡፡
እንግዲህ ሓጂ ሙሐመድ ሣኒ ማለት ያንን የቁርኣን ትርጉም ካበረከቱልን ሁለት ብርቅዬ ዑለማእ አንዱ ናቸው (ሼኽ ሰይድ ሙሐመድ ሳዲቅም የሃጂ ሣኒን ያህል ትልቅ ገድል ያላቸው ዓሊም ናቸው፤ እርሳቸውንም ወደፊት እንዘክራቸዋለን፤ ኢንሻ አላህ)፡፡
—–
 ሓጂ ሙሐመድ ሣኒ ሐቢብ የሚጠቀሱበት ሌላው ታሪክ የኢትዮጵያው መጅሊስ እንዲመሰረት ያደረጉት ተጋድሎ ነበር፡፡ በንጉሡ ዘመን መጅሊስ የሚባል ነገር አይታወቅም(“መጅሊስ” ይቅርና ዐረፋና ዒድ አልፈጥርም አይከበሩም ነበር)፡፡ በመሆኑም የኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞችን መብትና ጥቅም በጋራ የሚያስከብር ተቋም አልነበረም፡፡ ሙስሊሞችን ወክሎ የሚናገር፣ የሃጂና ዑምራ ጉዞአቸውን የሚያቀላጥፍ፣ መስጂዶችንና አውቃፍን የሚገነባና የሚያስተዳድር ተቋም ያስፈልግ ነበር፡፡ ሓጂ ሙሐመድ ሣኒ ከሌሎች ዑለማ ጋር በመሆን ሙስሊሞች የራሳቸው ተቋም እንዲኖራቸው ለረጅም ጊዜ ይሟገቱ ነበር፡፡ የ1966ቱ አብዮት ሲፈነዳ ህዝበ ሙስሊሙ መብቱ እንዲከበርለት የሚጠይቀውን የሚያዚያ 20/1966 ታላቅ ህዝባዊ ሰልፍ አደረገ፡፡ ሃጂ ሙሐመድ ሳኒ ሐቢብም የመጅሊሱን ጉዳይ ይዘው ከመንግሥት ጋር መሟገታቸውን ቀጠሉ፡፡ በአላህ ፈቃድ ትግሉ ሰምሮ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በብሄራዊ ደረጃ ተቋቋመ፡፡ ሓጂ ሣኒም ይህንን ተቋም እስከ እለተ ሞታቸው ከመሩት በኋላ በ1981 አረፉ፡፡ አላህ ስራቸውን ይውደድላቸው፡፡
—–
——
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
  “ሻዕቢያ” የሚለው ስም ሲነሳ የዑስማን ሳልህ ሳቤ ስምም አብሮ ይነሳል፡፡ በእርግጥም “ሻዕቢያ” የሚለውን ስያሜ በስራ ላይ ከማዋል ጀምሮ ድርጅቱን በሁለት እግሩ እንዲቆም ያደረገው ሳልህ ሳቤ በመሆኑ እርሱን እንደ ሻዕቢያ መስራች መመልከቱ አግባብ ነው፡፡ የ“ጀብሃ” ስም ሲጠቀስ ደግሞ ብዙዎች የሚያስታውሱት ሓሚድ ኢድሪስ አዋቴን ነው፡፡ ሆኖም ስህተት ነው፡፡ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ በታሪክ የሚታወሰው ጀብሃ የትጥቅ ትግል በጀመረበት ጊዜ የመጀመሪያውን ጥይት የተኮሰ ሰው በመሆኑ ነው፡፡ “ጀብሃት ታሕሪረል ኤርትሪያ” (በአጭሩ “ጀብሃ”) ወይንም በትግርኛ ስሙ “ተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ” (ተ.ሓ.ኤ) የሚባለው የኤርትራ አንጋፋ የፖለቲካ ድርጅት የተመሰረተው ግን ሃሚድ አዋቴ ትግሉን በባርካ በረሃ ከመጀመሩ ከአንድ ዓመት አስቀድሞ ነው፡፡ የድርጅቱ መስራቾች በአብዛኛው በካይሮ የሚማሩ ተማሪዎች ሲሆኑ የቀድሞው የኤርትራ ፓርላማ አባላት የሆኑ ጥቂት ሰዎችና ነጋዴዎችም ተቀላቅለቸዋል፡፡ ከመስራቾቹ መካከል ሙሐመድ ሳሊህ ሁመድ፣ ሙሐመድ አደም ኢድሪስ፤ ሰዒድ ሁሴን፣ ጣሓ ሙሐመድ ኑር፣ ወዘተ…ይጠቀሳሉ፡፡ ይሁንና እነዚህን ሰዎች አሰባስቦ የድርጅቱን መሰረት በመጣል ከፍተኛ ሚና የተጫወተው ሰው ኢድሪስ ገላውዴዎስ ይባላል፡፡

ኢድሪስ ዑሥማን ገላውዴዎስ በ1934 በከረን ከተማ አቅራቢያ በነበረችው “በይት ጀክ” በተባለች አነስተኛ ከተማ ነው የተወለደው፡፡ ኢድሪስ የቤኒአምር (ትግረ) ብሄረሰብ ነው፡፡  አባቱ ሀብታም ነጋዴ የነበሩ ከመሆኑም በላይ በተጨማሪም በምዕራባዊው ኤርትራ ሰፊ እርሻ ነበራቸው፡፡ በመሆኑም ኢድሪስ መደበኛ ትምህርቱን የጀመረው በ1942 የአባቱ እርሻ በሚገኝባትና በኢትዮጵያና ኤርትራ ድንበር ላይ ባለችው የአሊጊደር ከተማ ነው፡፡ በ1947 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ወደ ከሰላ (ሱዳን) ተላከ፡፡ የፖለቲካ ተሳትፎውንም የጀመረው በከሰላ ከተማ በነበረበት ወቅት ነው፡፡

  እንደሚታወቀው በዚያ ዘመን ኤርትራ በእንግሊዞች አስተዳደር ስር ነበረች፡፡ በዘመኑ ኤርትራ ነጻ መውጣት አለባት የሚሉና ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር ትቀላቀል የሚሉ ሁለት ጎራዎች ነበሩ፡፡ የመጀመሪያውን ጎራ የሚያንቀሳቅሰው “ራቢጣ አል-ኢስላሚያ” የሚባል ፓርቲ ሲሆን ሁለተኛውን ጎራ የሚመራው ደግሞ “ማሕበር ሀገር ፍቕሪ” የሚባለው ቡድን ነው፡፡ የኢድሪስ አባት የራቢጣ አባል የነበሩ እንደመሆናቸው “ኤርትራ ነጻ ትሁን” በማለት ከሼኽ ሱልጣን ኢብራሂም ጋር ብዙ ተንቀሳቅሰዋል፡፡ ኢድሪስም በአባቱ ላይ ባየው የትግል መንፈስ በጣም ተማረከ፡፡ መሆኑም “የራቢጣ” የወጣቶች ክንፍ አባል ሆነ፡፡

ኢድሪስ በ1951 ትምህርቱን በከፍተኛ በማዕረግ በማጠናቀቁ ከካይሮ ዩኒቨርሲቲ የስኮላርሺፕ እድል አገኘ፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲው ገብቶም የህግ ትምህርት ማጥናት ጀመረ፡፡ ከዓመት በኋላም የኤርትራ ተማሪዎች ማህበር ሲመሰረት የማህበሩ ሊቀመንበር ሆኖ ተመረጠ፡፡ ኢድሪስ በዚህ ማህበር ኤርትራዊያ ስደተኞችን ለማሰባሰብ በሰፊው ተጠቅሞበታል፡፡

   *****

ኢድሪስና ጓዶቹ በስደት ላይ ሆነው የሀገር ቤቱን ሁኔታ በቅርበት ይከታተሉት ነበር፡፡ በተለይም የተባበሩት መንግሥታት ለኤርትራ የሰጠው የፌዴሬሽን መብት እየተሸረሸረ ነው በማለት ተቃውሞአቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ በ1957 የኤርትራ ሰንደቅ ዓላማ ታገደ፡፡ ከዓመት በኋላም ትግርኛና ዐረብኛ የስራ ቋንቋ መሆናቸው አብቅቶ በአማርኛ ሲተኩ ደግሞ “ሐረካ” (Eritrean Liberation Movement) የተባለው ድርጅት በሚስጢር ተመሰረተ፡፡ ”

  የሐረካ ዓላማ ፌዴሬሽኑ በተቀመጠለት ደንብ መሰረት እንዲሰራ መጠየቅና ለዚህም እስከ መጨረሻው መታገል ነበረ፡፡ በተጨማሪም የትጥቅ ትግልን እንደ አማራጭ አልወሰደም፡፡ ይህ ድርጅት በካይሮ የነበሩትን ተማሪዎች በአባልነት ለማሳተፍ ሲሞክር ግን ተቃውሞ ገጠመው፡፡ እነ ኢድሪስ ገላውዴዎስ የሐረካ ዓላማና የትግል ስልት አዋጪ መስሎ ስላልታያቸው ድርጅቱን እንደ ከንቱ ማህበር ነበር ያዩት፡፡

   *****

 በ1960 ነው፡፡ ኤርትራዊያን በፌዴሬሽኑ አሰራር ሙሉ በሙሉ ተስፋ ቆርጠዋል፡፡ በርካቶቹም በአጼ ኃይለ ሥላሤ መንግሥት የተሾሙት ቢትወደድ አስፋሓ ወልደሚካኤል ለባርነት ሊዳርገን ነው እያሉ መነጋገር ጀምረዋል፡፡ ከዓመት በፊት የኤርትራ ሰራተኞችና ተማሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት የጸጥታ ሃይሎች በወሰዱት እርምጃ ሳቢያ በሀገር ቤት ተቃውሞ ማድረጉም ብዙ እንደማያራምድ አምነዋል፡፡ በዚህም የተነሳ በርካቶች የመንግሥትና የፓርላማ ስልጣናቸውን በመተው ወደ ውጪ መሰደድ ጀመሩ፡፡ እነዚህ ስደተኞች ካይሮ ከሚገኙት ተማሪዎች ጋር ከተቀላቀሉ በኋላ ስለ ድርጅት ምሥረታ መነጋገር ጀመሩ፡፡ ውይይቱም ፍሬያማ ሆኖ በመውጣቱ በጁላይ ወር 1960 ከነጻነት በስተቀር የፌዴሬሽንን ፎርሙላ የማይቀበል አዲስ ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ይህም ድርጅት “ጀብሃት ታሕሪረል ኤሪቲሪያ” ወይንም “ተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ” (ተ.ሓ.ኤ) ተብሎ ተሰየመ፡፡
     
   “ጀብሃ” ሲመሰረት የድርጅቱ ሊቀመንበር ሆኖ የተመረጠው የቀድሞ የፓርላማ አባል የነበረው ኢድሪስ ሙሐመድ አደም ነው፡፡ የድርጅቱ ዋና ጸሐፊ ደግሞ ኢድሪስ ገላውዴዎስ ነው፡፡ የድርጅቱ ላዕላይ ምክር ቤት (Supreme Council) አባላት ኢድሪስ ሙሐመድ አደም፤ ኢድሪስ ገላውዴዎስ፣ ሙሐመድ ሳሊሕ አሕመድ፣ ዑሥማን ኢድሪስ ኪያር፣ ሙሐመድ ሰዒድ ኪያር፣ ሲሆኑ ከአንድ ዓመት በኋላም ዑሥማን ሳልህ ሳቤ ተቀላቅሎአቸዋል፡፡
  
 “ጀብሃ” ከተቋቋመ በኋላ በምዕራብ ኤርትራ በረሃ በተበታተነ ሁኔታ ከሚታገሉት እነ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴን መከሳሰሉ ፋኖዎች ጋር ተገናኘ፡፡ ለአዋቴም የግንባሩን ወታደራዊ ክፍል እንዲመሩ ውክልና ሰጣቸው፡፡ በመስከረም 1/1961 በሃሚድ አዋቴ አዝማችነት በጀብሃ ስም የትጥቅ ትግሉ ተጀመረ፡፡ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ ከአንድ ዓመት በኋላ ሲገደሉ ደግሞ የወታደራዊውን ክንፍ የመምራቱ ስልጣን ለኢድሪስ ገላውዴዎስ ተሰጠ፡፡ በዚህም የኢድሪስ ገላውዴዎስ መቀመጫ ከካይሮ ከተማ ወደ ሱዳኗ ከሰላ ከተማ ተቀየረ፡፡

ኢድሪስ ገላውዴዎስ ከሰላ ከደረሰ በኋላ በሱዳን ውስጥ የሚገኙ ኤርትራዊያን ስደተኞችን እያሰባሰበ ወታደራዊ ስልጠና እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ በኋላ ላይ ደግሞ ለድርጅቱ ድጋፍ ለማግኘት ወደ ልዩ ልዩ ሀገራት ተጉዟል፡፡ በዚህም ውጤት አግኝቶበታል፡፡ ለምሳሌ በ1967 ወደ ቻይና ተጉዞ እነ ማኦ ዜዱንግን በማሳመን ለጀብሃ የመሳሪያና የስልጠና ድጋፍ አስገኝቷል (በዚያን ጊዜ ወደ ቻይና ሄደው ስልጠና ካገኙት መካከል አንዱ የአሁኑ የኤርትራ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ናቸው)፡፡ ወደ ኩባ በመሄድም የጀብሃ ተዋጊዎች የፓራ-ኮማንዶ ስልጠና እና የመሳሪያ ድጋፍ እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ ከሶሪያና ከኢራቅም ብዙ እርዳታ አስገኝቷል፡፡ የእስያ-አፍሪቃ የወዳጅነት ኮንፈረንስ በተካሄደበት ጊዜም ድርጅቱን በመወከል ተሳትፏል፡፡

   *****

ከዚህ ቀደም በጻፍኳቸው ጽሑፎች እንደገለጽኩት “ጀብሃ” የሚባለው ድርጅት በኤርትራዊያን ክርስቲያኖች ላይ ውገና ያካሄድ ነበር፡፡ የዚህም መነሻ “ለኃይለ ሥላሤ መንግሥት አሳልፈው የሸጡን ክርስቲያኖቹ ናቸው” የሚለው የተሳሳተ ፍረጃው ነው፡፡ እርግጥ የኃይለ ሥላሤ መንግሥት ኤርትራዊያን ሙስሊሞች ወደ ስልጣነ-መንግሥቱ እንዳይቀርቡ አድርጓል፡፡ በመንግሥት ስልጣንም ሆነ በፓርላማው ውስጥ የተሰገሰጉት በአብዛኛው ደገኛ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ ይሁንና የእነዚህ ጥቂት ሰዎች ምግባር ሁሉንም የኤርትራ ህዝበ ክርስቲያን አይወክልም፡፡ ስለዚህ ጀብሃ ኤርትራዊያን ክርስቲያኖችን በጥርጣሬ ማየቱና በድርጅቱ ውስጥ የነበሩትንም እያሳደደ መምታቱ ትክክል አልነበረም፡፡ ድርጅቱንም ለውድቀት ያበቃውም ይህ የውገና አቋሙ ነው፡፡

  ይህ ወገንተኛ አቋም የሁሉም የጀብሃ አባላት አቋም አልነበረም፡፡ በመሆኑም በ1969 በወታደራዊ ግንባር የተሰለፉት አባላት ፓርቲው ራሱን እንዲፈትሽና እንዲያሻሽል የሚቀሰቅሰውን የአዶብሃ ኮንፈረንስ ጠሩ፡፡ በኮንፈረንሱ ማጠቃለያም ድርጅቱ ራሱን እስካላሻሻለ ድረስ ካይሮ የሚገኘው ላዕላይ ምክር ቤት የሚያወጣቸውን መመሪያዎች እንደማይቀበሉ አስታወቁ፡፡ የካይሮው ምክር ቤት ኮንፈረንሱን በህገ-ወጥነት ፈረጀው፡፡ ሆኖም በከሰላ የሚገኘው ኢድሪስ ገላውዴዎስ የተነሱትን ጥያቄዎች እንደሚቀበል አስታወቀ፡፡ በዚህም የተነሳ ኢድሪስ ገላውዴዎስ ከአመራሩ ጋር ተጋጨ፡፡ በድርጅቱ ውስጥ የነበረውንም ከፍተኛ ስልጣን አጣ፡፡ ይሁንና የወታደራዊ ኮሚቴ ሊቀመንበርነቱን አልተወውም፡፡
 
 ኢድሪስ ገላውዴዎስ የጀብሃን ወታደራዊ ክንፍ በሚመራበት ወቅት ነበር በዑሥማን ሳልህ ሳቤ እና በኢሳያስ አፍወርቂ የሚመሩት ቡድኖች ከድርጅቱ ተንገጥለው የወጡት፡፡ የጀብሃ አመራር እነዚህን ቡድኖች በወታደራዊ ጥቃት የማጥፋት ውሳኔ አሳለፈ፡፡ ኢድሪስ ገላውዴዎስ ግን ውሳኔው ኤርትራዊያንን የበለጠ ይከፋፍላል በማለት ተቃወመው፡፡ ወታደራዊ ዘመቻዎችንም እንደማያስፈጽም ለድርጅቱ መሪዎች ቁርጡን ነገራቸው፡፡ በዚህም የተነሳ የድርጅቱ መሪዎች ኢድሪስን ከወታደራዊ መሪነቱ አስነሱትና በውጪ ጉዳይ ላይ ሾሙት፡፡

ኢድሪስ ገላውዴዎስ ድርጅቱን በውጪ ጉዳይ ሃላፊነት በሚመራበት ወቅት ድርጅቱ በጣም እየተዳከመ ነበር፡፡ ቢሆንም ኢድሪስ በውጪው ዓለም የድርጅቱን ስም የሚያስጠሩ ስራዎችን ሰርቷል፡፡ ለምሳሌ እ.ኤ.አ. በ1978 ታላቋ ሶቭየት ህብረት ጀብሃ ከደርግ መንግሥት ጋር እንዲወያይ በፈጠረችው መድረክ ላይ ድርጅቱን ወክሎ ተገኝቷል፡፡

 ከጥቂት ዓመታት በኋላ ጀብሃ ፍርስርሱ ወጣ፡፡ በኤርትራ ምድር የቀረው ትርፍራፊ ጦሩ በሻዕቢያ ተደመሰሰ፡፡ ድርጅቱም በስም ያለ በተግባር ግን የሌለ ሆኖ ቀረ፡፡ ይህንን የተመለከተው ኢድሪስ ገላውዴዎስ በድርጅቱ መሪዎች ላይ ከፍተኛ ሂስ ጽፎ አቀረበ፡፡ ድርጅቱ ሁሉንም ኤርትራዊያን በእኩል ሁኔታ አለማየቱና ዲሞክራሲያዊ አሰራር የሌለው መሆኑ ለሞት እንዳበቃው አሰመረበት፡፡ በመሆኑም ከጀብሃ አመራር ራሱን አገለለ፡፡

   በ1991 ሻዕቢያ ኤርትራን ሙሉ በሙሉ ሲቆጣጠር ኢድሪስ ገላውዴዎስ ለአዲሱ መንግሥት እውቅና እንደሚሰጥ አስታወቀ፡፡ እነ ኢሳያስ አፈወርቂም ወደ ሀገር መጥቶ በስራ እንዲረዳቸው ጥሪ አቀረቡለት፡፡ ኢድሪስም ግብዣውን ተቀብሎ ወደ ሀገር ውስጥ ገባ፡፡ ከ1991-1993 በነበሩት ዓመታትም ከዶ/ር በረከት ሃብተ ሥላሴ ጋር የሪፈረንደም ኮሚሽን ሃላፊ ሆኖ ሰራ፡፡ በተከታዮቹ ዓመታት ደግሞ የህገ-መንግሥት አርቃቂ ኮሚሽን አባል ሆኖ በመስራት ላይ እያለ እ.ኤ.አ በ1998 አረፈ፡፡ የቀብር ስርዓቱም በብሄራዊ ደረጃ ተፈጸመለት፡፡

   *****

   የጀብሃ አባላት ለኢድሪስ ገላውዴዎስ ሁለት ዓይነት እይታዎች ነው ያላቸው፡፡ ኢድሪስ ድርጅቱን ለመመስረትና የወታደራዊ ክንፉን መሰረት ለመጣል ያደረገውን አስተዋጽኦ በበጎ ዐይኑ ይመለከቱታል፡፡ ከዚያ በኋላ ግን አድርባይ ሆኖ ድርጅቱን ከድቷል በማለት ይኮንኑታል፡፡ የሻዕቢያ አባላትና ደጋፊዎች ግን ኢድሪስ ገላውዴዎስን በበረሃ ውስጥ የተገኘ ተክል አድርገው ነው የሚያዩት፡፡ “ጀብሃ ከውጥኑ ጀምሮ በርሱ ቢመራ ኖሮ ኤርትራዊያን እርስ በራሳቸው አይጋደሉም ነበር” በማለትም ያምናሉ፡፡ ሐቁ የትኛው እንደሆነ ታሪክ ነው የሚፈርደው፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ግን ኢድሪስ ገላውዴዎስ ማለት ከላይ የተገለጸው ሰው ነው፡፡
—–
ምንጮች

1.      www.awate.co,

2.     www.asmerino.com

3.     Tekste Negash: Ethiopia and Eritrea: The Federal Experience, 1997


(አፈንዲ ሙተቂ)
—-
     ጎንደር ካፈራቻቸው ሰዎች መካከል አብዛኛው ኢትዮጵያዊ የሚያውቀው እኝህ ሰው ይመስሉኛል፡፡ እኔ ጸሐፊው ስለርሳቸው የሰማሁት የቋራው መይሳው ካሳን ከማወቄ በፊት እንደሆነ አስታውሳለሁ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በአለቃ ገብረሃና ስም የሚነገሩ ቀልዶችን የነገረን ደግሞ ማን መሰላችሁ….? ከዚህ በፊት ያስተዋወቅኳችሁ የሁለተኛ ክፍል አለቃችን የነበረው አያሌው አብነት  ነው፡፡ ሆኖም እርሱ ያኔ የነገረንን እዚህ መጻፍ አይመችም፡፡ ስለዚህ የአያሌውን ቀልዶች ትተን ስለአለቃ ገብረሃና ከመዛግብት ያገኛቸውን ወጎች እንጨዋወታለን፡፡ ከዚያ በፊት ግን “ዐረፈ ዐይኔ ሐጎስ” “አለቃ ገብረሃ እና አስቂኝ ቀልዶቻቸው” በሚል ርዕስ ካሳተሙት መጽሐፍ ያገኘነውን የአለቃ ገብረሃናን ታሪክ አጠር አድርገን እናወሳለን፡፡
  
አለቃ ገብረሃና በሙሉ ስማቸው “ገብረሃና ደስታ ተገኝ” ይባላሉ፡፡ የተወለዱት በ1814 በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብ ታቦር አውራጃ ፎገራ ወረዳ (አሁን ደቡብ ጎንደር ዞን ፎገራ ወረዳ) ውስጥ ነው፡፡ በተወለዱበት አካባቢ የቤተ ክህነት ትምህርት ተምረው በሃያ ስድስት ዓመታቸው የሊቀ-ካህናት ማዕረግ አግኝተዋል፡፡ በዚህ ሹመት ለሰባት ዓመታት ካገለገሉ በኋላ በፍትሐ ነገሥት አዋቂነታቸው ተመርጠው ጎንደር ውስጥ በዳኝነት ተሾሙ፡፡
  አለቃ በካህንነትም ሆነ በዳኝነት ሲያገለግሉ እንደ ሌሎች የዘመኑ መኳንንት ቁጥብ አልነበሩም፡፡ ከተራው ህዝብም ሆነ ከመንግሥት ባለስልጣናት ጋር ይቃለዱ ነበር፡፡ ይህ ቀልደኝነታቸው እየገነነ ሄዶ በትንሹ ራስ ዓሊ ዘንድ ተሰማላቸው፡፡ በመሆኑም ወደ ቤተ መንግሥት ተጠርተው የራስ ዓሊ አጫዋች በመሆን ተሰየሙ፡፡ እንግዲህ ከዚህን ጊዜ ጀምሮ ነው አለቃ ገብረሃና የመኳንንቱና የመሳፍንቱ አጫዋች በመሆን ህይወታቸውን የገፉት፡፡
 
   አለቃ ገብረሃና በአጼ ዮሐንስም ሆነ በአጼ ምኒልክ ዘንድ ክብርና ሞገሥ አግኝተው እንደ ታላቅ ሰው ይታዩ ነበር፡፡ በአጼ ቴዎድሮስ ዘመን ግን ከፍተኛ ችግር ደርሶባቸው ነበር፡፡ ቴዎድሮስ አለቃን ያገኟቸው በቤተ መንግሥቱን ከራስ ዓሊ በተረከቡ ጊዜ ነው፡፡ ቴዎድሮስ አለቃን በዝና ቢያውቋቸውም ቀልድና ባልቱን አልወደዱላቸውም፡፡ ቴዎድሮስ ቀልዱን እንዲያቆሙና በዳኝነቱ እንዲቀጥሉ ቢገስጿቸውም አለቃ በጄ የሚሉ አልሆኑም፡፡ በመሆኑም አለቃን ከዳኝነታቸው ሽረው ትግራይ ውስጥ የሚገኘው የጨለቆት ሥላሤ ገዳም አስተዳዳሪ አድርገው ሾሟቸው፡፡ 
  
የደብሩ ቆይታ የቤተ መንግሥት ኑሮ ለለመዱት አለቃ ገብረሃና የሚመች አልሆነም፡፡ በዚያ ላይ አጼ ቴዎድሮስ ቤተ ክህነትን ርስት አልባ ለማድረግ መሞከራቸው ከሀገሬው ህዝብ ጋር አጣላቸው፡፡ በመሆኑም ካህናቱ ቴዎድሮስን ለመገልበጥ ማሴር ጀመሩ፡፡ አለቃ ገብረሃናም ዱለታውን ተቀላቀሉ፡፡ ይህም ወሬ ለአጼ ቴዎድሮስ ደረሳቸው፡፡ አጼውም አለቃ ገብረሃና ታስረው እንዲቀርቡ አዘዙ፡፡ ሆኖም አለቃ ገብረሃና ሸሽተው ጎጃም ውስጥ ከሚገኘው ዘጌ ገዳም ተደበቁ፡፡
   ከሁለት ዓመት በኋላ አጼ ቴዎድሮስ በመቅደላው ጦርነት ራሳቸውን ገደሉ፡፡ አለቃ ገብረሃናም ከተደበቁበት ወጥተው ወደ ጎንደር ተመለሱ፡፡ በ1864 አጼ ዮሐንስ አራተኛ ሲነግሡ በጎንደር ከተማ የነበራቸውን የቀድሞ ሹመታቸውን አጸደቁላቸው፡፡ በምኒልክ ጊዜ ደግሞ ወደ አዲስ አበባ መጥተው በእንጦጦ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን የአቋቋም እና የመርገድ አስተማሪ ሆኑ፡፡ ከጥቂት ቆይታ በኋላም የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ሆኑ፡፡
  አለቃ ገብረሃና በአዲስ አበባ ኑሮአቸው ከአጼ ምኒልክ ጋር ተዋድደው ይኖሩ ነበር፡፡ ነገር ግን እቴጌ ጣይቱ ቀልዳቸውንና ተረባቸውን አልወደዱላቸውም፡፡ በዚህም የተነሳ ሁለት ጊዜ ተጣልተው ወደ ደብረ ታቦር ሄደዋል፡፡ በሶስተኛው ዙር ግን ከአጼ ምኒልክም ጋራ ተቀያይመው ኖሮ እስከ መጨረሻው ተሰነባብተው ወደ ትውልድ ቄየአቸው ከሄዱ በኋላ እዚያው ኖረው በሰማኒያ አራት ዓመታቸው አርፈዋል፡፡
  አለቃ ገብረሃና መልከ መልካም ቢሆኑም አጭር ሰው ነበሩ፡፡ በዚህ ቁመታቸውም ከሌሎች ጋራ ብዙ ጊዜ ተቋስለዋል፡፡ አንዳንዶች ደግሞ በእግራቸው መንሻፈፍ ሊቀልዱ ሲሞክሩ አለቃ ያልጠበቋቸውን መልሶች እየሰጧቸው “ኩም” ያደርጓቸው ነበር፡፡
   አለቃ ወይዘሮ ማዘንጊያ ከተባሉት ባለቤታቸው ተክሌ የተባለ ልጅ ወልደው ነበር፡፡ ይህ ልጃቸው በትምህርት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶ የደብረ ታቦር እየሱስ ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን ካህን እስከ መሆን ደርሷል፡፡ ሆኖም ጠላቶቹ ተመቀኝተውት መድኃኒት በጥበጠው በማጠጣት ገድለውታል፡፡
   *****
    በአለቃ ገብረሃና ስም የሚነገሩ ብዙ ጨዋታዎችና ቀልዶች አሉ፡፡ አንዳንዶቹ በርሳቸው የተነገሩ መሆናቸው የተጻፈ ቢሆንም አንዳንዶቹ በጊዜ ሂደት የተፈጠሩ ናቸው፡፡ ለበረካ ያህል በርሳቸው ስም የሚነገሩ ጥቂት ጨዋታዎችን እንቋደስ፡፡
   አንድ ጊዜ አለቃ ለግብዣ ተጠሩ፡፡ በግብዣው የቀረበው ጎመን ሆዳቸውን ቆዝሮአቸው ኖሮ ወደ እሳት ዳር ተጠጉና ሆዳቸውን ማሻሸት ጀመሩ፡፡ ጋባዣቸው ነገሩ ገርሞት “ምነው አለቃ! ሆድዎትን ምን ሆነው ነው” ሲላቸው “ረ ምንም አይደለም! ጎመኑን እያበሰልኩት ነው” በማለት መለሱላቸው፡፡
  በሌላ ጊዜ ደግሞ አለቃ የታመመ ሰው ሊጠይቁ ይሄዳሉ፡፡ የቤቱ ባለቤት ጠላ ትሰጣቸውና ታቀርብላቸዋል፡፡ አለቃ ጠላውን ፉት እያሉት ሳሉ ሴትዮዋ አመለጣት፡፡ አለቃ ጠላቸውን አገባደው ሲጨርሱ ሴትዮዋ ወደርሳቸው መጣችና “ልድገምዎት እንዴ አለቃ” በማለት ጠየቃቸው፡፡ አለቃም “አዎ! ግን እንደ ቅድሙ ጠረር አታድርጊው” አሏት፡፡
    አለቃ ስንቃቸውን በአገልግል ይዘው ከጥቂት ነጋዴዎች ጋር የዐባይ በረሃን በማቋረጥ ላይ ሳሉ ሽፍቶች በአካባቢው እንዳሉ ይሰማሉ፡፡ ነጋዴዎቹም ለገንዘባቸው አለቃም ለነፍሳቸው ተጨነቁ፡፡ “ምን እናድርግ” እያሉ በመመካከር ላይ ሳሉ አለቃ አንድ ዘዴ ትዝ ይላቸውና ነጋዴዎቹ ገንዘባቸውን እንዲሰጧቸው ይጠይቁአቸዋል፡፡ ነጋዴዎቹም የተጠየቁትን አደረጉ፡፡ አለቃም ገንዘቡን ከአገልግላቸው ውስጥ ከተቱት፡፡
    ጥቂት እንደተጓዙ ሽፍቶቹ ከጫካ ውስጥ ወጥተው “ያላችሁን ቁጭ አድርጉ” ይሏቸዋል፡፡ ነጋዴዎቹ ምንም የለንም ይላሉ፡፡ ሽፍቶቹ ወደ አለቃ ዞረው “በአገልግሉ ውስጥ ያለው ምንድነው” ብለው ጠየቋቸው፡፡ ብልሃተኛው አለቃ “ወላሂ! ወላሂ! ክሽን ያለች የዶሮ ወጥ ናት! ከፈለጋችሁ እዚሁ እንብላ” ብለው መለሱ፡፡ ሽፍቶቹም “በስመ አብ! እኛ የእስላም ስጋ አንበላም” እያሉ በማማተብ ለቀቋቸው፡፡
——
አፈንዲ ሙተቂ)
ታሕሳስ 2007


(አፈንዲ ሙተቂ)
—–አንድ–ኡምዱርማን (ሱዳን)—
አሕመድ ያ ሐቢቢ ሰላም ዐለይከ
ያ ሚስኪ ወጢቢ ሰላም ዐለይከ
ሰላም ዐለይከ ዘይነል አንቢያእ
ሰላም ዐለይከ አትቀል አትቂያእ
ሰላም ዐለይከ አስፈል አስፊያእ
ሰላም ዐለይከ ሚን ረብቢ ሰማእ
ሰላም ዐለይከ ዳኢማን ቢላ ኢንቲሃእ
——ሁለት–ገለምሶ—
1.      ሙሐመድ ሰላሙን ዐለይኩም
ሰይዲ ሰላም ዐለይኩም
ሰለዋቱላህ ዐለይኩም
2.     አላሁመ ሰሊ ዐላ ሰይዲና ሙሐመዲን ወዐላ ኩልሊ ነቢዪን
ወሰልሊ ዐላ አቢበክሪን ወዐላ ኩልሊ ወሊዪን
ወሰልሊ ዐላ ጂብሪለን ወዐላ ኩሊ መለክ
—-ሶስት– ጅማ—
አላህ አላህ ላኢላሀ ኢልለላህ
 ሙሐመዱን ረሱሉላሂ ሐቢቡ ዒንደላህ
ዐለይሂ ሰላቱ ወሰላሙ ሚነልላህ
—-አራት– ጅቡቲ—-
ሰላዋቱልላህ ዐለይከ ያ ሙሐመድ
ሰላሙልላህ ዐለይከ ያ ሙሐመድ
ሰላሙልላሂ ያ ኑረል ቁሉቢ
ያ ኑረል ቁሉቢ
—-አምስት– ሐረሪ—–
ሰሊ ያ ረብቢ ዐላ ሙሐመዲን
ሰሊም ያ ረብቢ ዐላ ሙሐመዲን
ባሪክ ያ ረብቢ ዐላ ሙሐመዲን
ኩሉ የውሚን ወለያሊን አልፈ መር
—-ስድስት– ወሎ—– 
ሰላቱ ወተስሊሙ ወ አዝካ ተሒቲን
ዐለል ሙስጠፈል ሃዲ ጣሃ ያ ሙሐመዲን
——————————————–


ከበአበባየሁ ገበያው
 ——-
የሶሻሊዝምን ርዕዮተ ዓለም 1960ዎቹ ማብቂያ ላይ በአገራችን ያስተዋወቁት የደርግ ባለስልጣናት ሶሻሊዝምን የተረዱት 70 ዓመቱ አዛውንት የጐጃሙ ቆምጬ አምባው በተረዱት መንገድ ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያ ታሪክ አሁን ከምናየው ፍፁም የተለየ ይሆን ነበር፡፡ ለእሳቸው ሶሻሊዝም ማለት ሠርቶ ማሰራት ነበር፤ ሶሻሊዝም ሜዳ ተራራውን አረንጓዴ ማልበስ ነበር፤ ለእሳቸው ሶሻሊዝም ብዙ /ቤት፣ ክሊኒክ፣ ወፍጮ ቤት፣ መገንባት ሌባን ማጥፋት ነው፡፡ በደርግ ዘመን 13 ዓመት የተለያዩ ወረዳዎችን ያስተዳደሩት ቆምጬ፤ በሠሯቸው በርካታ የልማት ሥራዎችና ብልሃት በታከለበት የአመራር ችሎቻቸው ከመንግስትም ከህዝብም ተወዳጅነት እንዳገኙ ይናገራሉ፡፡ እሳቸው ያልተናገሯቸው ብዙ ነገሮች እየተፈጠሩ በስማቸው እንደሚነገሩ አዛውንቱ ቢናገሩም እራሳቸው በትክክል የፈፀሟቸውም ቢሆኑ ከፈጠራዎቹ የሚተናነሱ አይደሉም፡፡ በሃላፊነት በሚመሩት ወህኒ ቤት የነበሩትን በጣታቸው እየፈረሙ ደሞዝ የሚበሉ ያሏቸውን ፖሊሶች 60 ቀን ማንበብና መፃፍ እንዲማሩ የፈጠሩት ብልሃት ተጠቃሽ ነው፡፡ ኰሎኔል መንግስቱ /ማርያም በሥራቸው ተደስተው ሽጉጣቸውን ሲሸልሟቸው አልተቀበሉምከሽፍታ ያስፈታሁት 18 ሽጉጥ አለኝ በማለት፡፡ በምትኩ ግን ለህዝቡ መብራትና ውሃ እንዲገባለት ጠይቀዋል፡፡ በትውልድ አገራቸው በጐጃም ያገኘቻቸው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ሰፊ ቃለ-ምልልስ ያደረገችላቸው ሲሆን አንባቢያን የእኒህ መለኛ አብዮተኛ ታሪክ ከነለዛቸው ይደርሳቸው ዘንድ ቃለምልልሱን እንደወረደ አቅርበነዋልከአነጋገር ዘዬአቸው ጋር፡፡
——
የት ተወለዱ? መቼ?
የተወለድኩት በጠላት ወረራ ዘመን ነው፡፡ በጐዛምን ወረዳ ማያ አንገታም ቀበሌ ገበሬ ማህበር፣ አባላይ በተባለ ቦታ ሜዳ ላይ ተወለድኩ፡፡ እናቴም አባቴም አርበኛ ናቸው፡፡ ስወለድ ማን እንበለው እያሉ ሲመካከሩ ሳለ አንድ አውሮፕላን ትመጣና ክምር ስታቃጥል፣ አባቴ አነጣጥሮ ቢተኩስ ተንከታክታ ወረደች፡፡ ያን ጊዜ ቆምጬአምባው እንበለው፤ ይኼ ልጅ ገዳም ነው ተብሎ ነው ስም የወጣልኝ፡፡
ለትምህርት እንደደረስኩ እዚያው ቀበሌ አንገታም ጊዮርጊስ የቄስ ትምህርት ተምሬ፣ ዳዊት ፆመድጓ ጨርሼ ወደ ቅኔ ቤት ገባሁ፡፡ በሽታ እንደገባ አባቴ ከቅኔ ቤት አውጥተው ወሰዱኝ፡፡ 15 ዓመቴ የሰባት ደብር የጐበዝ አለቃ ሆንኩኝ፡፡
ቆምጬ ማለት ምን ማለት ነው?
ደፋር፣ ጠንካራ፣ ቆራጥ ማለት ነው፡፡
በሸዋ ግን ትርጉሙ ሌላ መሰለኝ. . .
አዎ፡፡ በእኔ በኩል ግን ቆምጬ ማለት ታይቶ የሚታለፈውን የሚያውቅ፣ ታይቶ የማይታለፈው ላይ ቆራጥ እርምጃ የሚወስድና ሩህሩህ፣ የዋህ ማለት ነው፡፡
ወጣትነትዎ እንዴት አለፈ?
በወጣትነቴ የቤተሰብ ተጽዕኖ ነበረብኝ. . . ሰው ፊት ጠላ መጠጣት አይፈቀድልኝም፤ ውሃ እንኳን ጭልጥ አድርጎ መጠጣት እንከለከላለን፡፡ ስንበላ አፋችሁን ገጥማችሁ አፋችሁን አታጩሁ፤ እየተባልን ነው ያደግነው፡፡ አባቴ ቅዳሴ አስቀድሼ ወጥቼ መሃራ አያስቀምጡኝም ነበር፡፡ ..መሃራ መብላት ያለበት አቅም ያጣ፣ ቤቱ የሚበላው የሌለው ነው፡፡ አንተ ሁሉ ነገር ቤትህ ሞልቶ የተረፈህ ስለሆንክ ምንም እንዳትቀምስ.. እባላለሁ፡፡ ሰርግ ስንሔድ የአባቴን መሣሪያ ይዤ ከበስተጀርባው ነበር የምቀመጠው፡፡ እህል በወሰክንባ(ሞሶብ) ነበር የሚመጣልኝ፡፡ ጨዋታ አምሮኝ ከጉብላሊቱ(ህጻናት) ጋር መደባለቅ አይፈቀድልኝም፡፡ ከፍተኛ ተጽዕኖ ነበረብኝ፡፡ በፆም ቀን ከስምንት ሰዓት በፊት ስንበላ ከተገኘን እንደበደባለን፡፡ የገና ጨዋታ፤ ፈረስ ግልቢያ፣ ዋና፣ አውሬ አደን ምን ልበልሽ ያልተሳተፍኩበት የለምከሁሉም ግን ደስ የሚለኝ አደን ነበር፡፡
ምን አድነዋል?
ድኩላው፣ አሳማው፣ ሚዳቋው. . . በለሴ ሆኖ ወደ እኔ ይመጣል፡፡ በቃ እያልን አገሬ ይዤ እገባለሁ፡፡ ከሰው የተጣላሁ እንደሆን አባቴ አይለቀኝም ነበር፡፡
የደብር አለቃ ሳለሁ ሰው ሲጣላ ባውቀውም ባላውቀውም አስታርቅ ነበር፡፡ በዚያውም የስብሰባን ጥቅምና የአንዳንድ ነገሮችን ሁኔታ ማየት ጀመርኩ፡፡
ስለትዳርና ቤተሰብ ይንገሩኝ. . .
አስር ልጆች አሉኝ፡፡ ባለቤቴ አሁን ያለችት የልጆቼ እናት ናት፡፡ ለሷ የእኔ እና የእሷን ስምንት ስምንት የቀንድ ከብት አማተን ደርሰን ሃብታም ሆነን፤ ኋላ ገንዲ በሽታ መጣና ከብቱን ሲፈጀው ተበሳጨሁና ወደ ጐጃም ጠቅላይ ግዛት መጣሁ፡፡ የምክትል ፀሃፊነት ፈተና ተፈተንኩና አለፍኩጃናቢት በተባለች ስፍራ፡፡
ደሞዙ ጥሩ ነበር?
25 ብር ነው፡፡ ማለፌን ከሰማሁ በኋላ አንድ አህያ ተልባ፣ አንድ አህያ ኑግ ጭኜ ወደ ደብረማርቆስ ገበያ ወጣሁና ቦጋለ በረዳ የሚባል ቦታ ሸጥኩት፡፡ ከዚያ ምክትል ፀሃፊነት አለፍኩ አልኩና ሁለት አዝማሪ ጥሩ ብዬ፣ ሹመቴን እያነሳሳ ሲዘፈን ሲጠጣ ሲበላ ታደረ፡፡ ጥቂት ብር ቀረችኝ፡፡ ማለዳ የሹመት ደብዳቤውን ልቀበል አውራጃ አስተዳደሩ ስሄድ የወረዳው ገዢ ቀኝ አዝማች ረታ ፈረደ ይባላሉ ..አንተ ነህ ምክትል ፀሃፊ የተሾምከው?.. አሉኝ፡፡ አለባበሴም ደህና ነው ያን ጊዜ፤ ንቁ ነኝ፡፡ ..አዎ.. አልኳቸው፡፡
..አንተማ የዋናው የከበርቴ ልጅ አይደለህ፤ ሰባት ጉልት እያሳረሳችሁ፤ አንተን አንቀጥርም! በል ውጣ ከቢሮዬ.. አሉኝ፡፡ ተበሳጨሁ ገንዘቤን ጨርሻለሁ፤ ሌላ አማራጭ ሳፈላልግ በደብረማርቆስ ወህኒ /ቤት ለወታደርነት ቅጥር የተለጠፈ ማስታወቂያ አየሁ፡፡ ወዲያው እለቱን ተመዝግቤ አለፍኩ፡፡ ሲያዩኝ በቁመትም በክብደትም እኩል መጣሁ፡፡ ወደ ማሰልጠኛ ላኩኝ፡፡ ከማረሚያ ቤት አስተዳደር ወታደሮች አስራ ሰባት፣ ከፖሊስ ሰባት ነበር የተመለመለው፡፡ እዚያ ተደባልቀን ስንማር በፀባይ፣ በተኩስ፣ ህግ በማወቅ አንደኛ ወጣሁ፡፡የዚያን ጊዜው አገረገዥ ደጅአዝማች ፀሃይ እንቁ ኃይለስላሴ፣ የምስክር ወረቀት ሲሰጡ ..በወታደራዊ አቋም፣ በፀባይና በተኩስ ወታደር ቆምጬአምባው ይልማ አንደኛ.. ብለው ሸለሙኝ፡፡ ኮሎኔል አሰፋ ወንድማገኘሁ ከሚባሉ ከወህኒ ቤቱ አዛዥ ጋር ጠሩኝና ..ከአስራ ሰባቱ ወታደር አንተ በጣም ጠንካራ ነህ፤ ወደፊትም እናሳድግሃለን.. አሉና ሃምሳ ብር በግሌ ሰጡኝ፡፡ የወህኒ ቤቱ /ቤት የእስረኞች የህግ አማካሪና የጠቅላይ ግዛቱ ወህኒ ቤት ጠበቃና ነገረ ፈጅ አደረጉኝ፡፡ ኮልት ሽጉጥም ሸለሙኝ፡፡
ከእስረኞች ጋር ስለነበርዎ ግንኙነት ያጫውቱኝ፡፡
እስረኛው አንዳንድ ጊዜ ..ምግብ ጠቆረ.. ይልና ያድማል፡፡ ..እኛ መነገጃ አይደለንም.. ይላል፡፡ የጐጃም ጠቅላይ ግዛት በሙሉ፣ 35 ወረዳና የሰባቱ አውራጃ እዚሁ ነበር የሚታሰረውየመተከል፤ የቤንሻንጉል፤ የባህርዳር ሁሉ ማለት ነው፡፡ እስረኛው ሲያድም እኔ ሽጉጥ ታጥቄ በመሃላቸው እገባና ..እናንተን ያሰራችሁ ሰው አይደለም፤ ያሰራችሁ እግዚአብሔር ነው፡፡ እዚህ እኮ የምትፀልዩበት፣ የምትማፀኑበት፣ ፍርድ እናግኝ ብላችሁ የምትለማመኑበት ነው፡፡ የጐጃም ሰው ሆዳም አይደለም ምግብ አነሰኝ ብሎ አይናገርም፡፡ አናንተ ቆሎ፣ በሶ፣ በግም ፍየልም አሳርዳችሁ ትበላላችሁ፤ አገራችን ተሰደበ.. ብዬ ያንን ጠቆረ አንበላም ብለው የተውትን ጥቁር እንጀራ እነሱ መሃል ሆኜ ቆርሼ እበላዋለሁ፡፡ ያንዜ ያጨበጭባሉ፡፡ ከዛ በኋላ አድማው ይበተናል፡፡ ..አሁን ትፈታላችሁ ግማሻችሁ በአመክሮ፤ ግማሾቻችሁ ደግሞ ፀባያችሁ ጥሩ ከሆነ ሚያዚያ 27 በአርበኞች ድል በዓል ወይም ሐምሌ 16 በጃንሆይ ልደትና ጥቅምት 23 በጃንሆይ የዘውድ በአል ትፈታላችሁ፡፡ እንቢ ካላችሁ ግን ችግር ላይ ትወድቃላችሁ.. ስላቸው በጀ ይላሉ፡፡ የጣቢያው አዛዥ ንግግር ስለማያውቅበት ቀጠሮ ስጡኝ ብዬ እኔ ነበርኩ የማናግራቸው፡፡
ለእስረኛው ያወጡት ህግ ነበር ይባላል?
ህጉ እያንዳንዱ እስረኛ ሰውነቱን በሳምንት አንድ ቀን ፀጉሩን ዕለት ዕለት እንዲታጠብ የሚል ነው፤ አሽቶ የሚያጥበው በወር 1 ብር ከፍሎ ሰው ራሱ ይቀጥራል፡፡ እስረኛው ገንዘብ ነበረው፡፡ ሞልቶታል፡፡ ከዚያ አሰልፋቸውና ከኪሴ ነጭ መሀረብ አውጥቼ የአንዱን ደረት አሸት አድርጌ ..ይሄው እድፍ አለው ውጣ.. እለዋለሁ፡፡ ንፁህ ሆኖ ያገኘሁትን ደግሞ አንድ ብር አወጣና እሸልመዋለሁ፡፡ ያን ጊዜ እስረኛው ሁሉ ንፁህ ለመሆን መሯሯጥ ነው፡፡ የመኝታቸውን ዳትም ክፍላቸው እየገባሁ እፈትሽ ነበር፡፡ ይሄን አይተው ደጃዝማች ፀሃይ (1958) የደ/ማርቆስ ቤተመንግስት ሲሰራ ..ይሄ ጐበዝ ልጅ ነው፤ ጠንካራ ሰራተኛ ነው.. ብለው ወሰዱኝና እንደገና ተሸለምኩ፡፡
ንጽህናውን ያልጠበቀ እስረኛስ? ቅጣት አለው?
አዎ ይቀጣል፡፡ አስር የችግኝ ጉድጓድ አስቆፍረዋለሁ፤ በግቢው ውስጥ የፍራፍሬና የአትክልት ስፍራ ስለነበረ እሱንም አስቆፍራቸዋለሁ፡፡ ሰው ገድሎ የታሰረውን ግን ወታደሩ ስራ አናሰራም ብሎ ይቃወመኛል፤ መሳሪያ ነጥቆን ይሄዳል በሚል፡፡ ..በያዝከው መሳሪያ አጨማደህ አትጥለውም፤ እንግዲህ በእግር ብረት ታስሮ አይሞትም.. እልና፤ የገደለውን ሁሉ ሰብስቤ .. ተንቀሳቀሱ ይሄ ስራ የእናንተ ነው፣ አካልና አእምሮአችሁን አስተባብራችሁ በሞራል የጠነከራችሁ እንድትሆኑ ስሩ.. እላቸዋለሁ፡፡ በጣም ይወዱኛል፡፡ /ቤት ለስራ ስሄድ ባዶ ወረቀት ካገኘሁ ሰብስቤ አመጣና አንዳንዱን በሽልማት እሰጣቸዋለሁ፤ ለዘመድና ለምሽት ደብዳቤ መጠጣፊያ፡፡ ከዚያ ፊደል ሠራዊት የሚባል መሰረተ ትምህርት ተቋቋመ፡፡ በደጃዝማች ፀሃይ ጊዜ፣ አቶ ሸዋቀና የተባሉ የትምህርት ሚኒስቴር ሃላፊ፣ የጠቅላይ ግዛቱን ወህኒ ቤት እሱ ነው ማስተባበር የሚችለው አሉና እኔን ሾሙኝ፡፡ ማንበብ መፃፍ የማይችል፤ በጣቱ እየፈረመ የሚበላ ፖሊስ ሞልቷልያኔ፡፡ አዳራሽ ላይ ሰበሰብኩና እስከ ስልሳ ቀን ድረስ ማንበብና መፃፍ ካልቻላችሁ ሚስጢር ነው የምነግራችሁ ..ትባረራላችሁ.. ተብሏል አልኳቸው፡፡ (ሳቅ) መንግስት አቋም ይዟል፤ ማታ ማታ ልጆቻችሁ ቤት ውስጥ ያስተምሯችሁ አልኳቸው፡፡ ማንበብ መፃፍ የማይችል ሠራዊት በፍፁም አይሆንም፤ እየተባለ ነው ስላቸው. . . ማታ ማታ ጥናት ነው፣ ማንበብ ነው፡፡ ሲፈተኑ ደህና ናቸው፡፡ ..ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዘኢትዮጵያ.. ብዬ ብላክ ቦርዱ ላይ ፃፍኩና ገልብጡ አልኳቸውእንዳለ ፃፉት፡፡ በዚህም ተሸለምኩ፡፡
አብዮቱ ሲፈነዳ በአንድ ቀበሌ ውስጥ ህዝቡ ስለሚያውቀኝ የአብዮት ጥበቃ የፍርድ ዳኛ ሸንጐ ውስጥ ገባሁ፡፡ በደብረማርቆስ በድሮው ቀበሌ 8 ዳኛ ሆንኩ፡፡ ስራዬ እርቅ ነበርይቅር ተባባሉ ማለት፡፡ ፍርድ የሚሻውን ደግሞ ፍርድ እያሰጠሁ እየቀጣሁ በሬድዮ አስነግራለሁ፡፡ ጉልታዊ አገዛዝን እየኮነንኩ፤ የሠራተኛውን መደብ ንቃ እያልኩ የተናገርኩRead more ›

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
በኢህአዴግ ዘመን ሲያገለግሉ ከነበሩት የኢትዮጵያ መንግሥት ባለስልጣናት መካከል በህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ከበሬታና ተወዳጅነት ያላቸው በፎቶው ላይ የምትመለከቷቸው ዶ/ር ተወልደ-ብርሃን ገብረእግዚአብሄር ናቸው፡፡ ዶ/ር ተወልደብርሃን በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ ላደረጉት ምርምርና በጉዳዩ ዙሪያ ከፍተኛ ግንዛቤ እንዲፈጠር ላደረጉት ጥረት በፈረንጆቹ 2000 ዓመት ዓለም አቀፉን የአቋራጭ ኖቤል ሽልማት (በትክክለኛ ስሙ Right Livlihood Award የሚባለውን) ተሸልመዋል፤ ይህንን ፎቶ የተነሱትም ሽልማቱን በተቀበሉበት ወቅት ነው፡፡ ዶ/ር ተወልደ በፈረንጆቹ 2006 ዓመትም የተባበሩት መንግሥታት በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ ሰዎች የሚሸልመውን Champions of the Earth ሽልማት አግኝተዋል፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም በ1997 የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥቶአቸዋል፡፡
እኚህ ሰው የሀገራችንን የብዝሀ-ህይወት ኢኒስቲትዩት ከማቋቋማቸውም በላይ ሀገር ዝርያቸው ለመጥፋት የተቃረበ ሀገር በቀል ዛፎችን በሰፊው በማጥናት ለዘራቸው ጥበቃ የሚደረግበት የኢትዮጵያ ጄኔቲክ ባንክ እንዲመሰረት ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ የሀገራችንን የአካባቢ ጥበቃ ፖሊሲ የቀየሱትም እርሳቸው ናቸው፡፡ በተጨማሪም ዶ/ር ተወልደ የአፍሪቃ ሀገራት የአሜሪካና የአውሮጳ ኩባኒያዎች ወደ ከባቢ አየር በሚለቋቸው በካይ ጋሶች ለሚደርስባቸው ጉዳት ተመጣጣኝ የካሳ ክፍያ እንዲጠይቁ ካስተባበሩት መሪዎች አንዱ ናቸው፡፡
—-
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን በትግራይ ክልል በአድዋ ከተማ አቅራቢያ ባለችው “አዲ-እስላም” የተሰኘች የገጠር መንደር ነው የተወለዱት፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በ1955 ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተቀበሉ በኋላ የማስትሬትና ዶክትሬት ዲግሬአቸውን ከዌልስ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፡፡ ዶ/ር ተወልደ በ1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሳይንስ ፋኩልቲ ዲን ሆነው አገልግለዋል፡፡ ከ1975 እስከ 1982 በነበረው ዘመን ደግሞ የአስመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሆነው ሰርተዋል፡፡ አስመራ በህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) ስትከበብ ደግሞ ወደ አዲስ አበባ መጥተው በያኔው ካቢኔ ውስጥ የባህል ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስትር ሆነው አገለገሉ፡፡ የደርግ መንግሥት ከተወገደ በኋላም ለብዙ ዓመታት በሚታወቁበት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተርነት አገልግለዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ከመንግሥት ስራ በጡረታ ተገልለው በግል ሙያ ላይ ተሰማርተዋል፡፡
  ይህንን ካልን ዘንዳ ዶ/ሩ የሚተቹበትን አንድ ነጥብ መጠቆም እንፈልጋለን፡፡ ከቅርብ ዓመታት ጀምሮ ከአውሮጳ የመጡ የአበባ አምራችና ላኪ ኩባኒያዎች ሀገራችንን አጥለቅልቀዋታል፡፡ እነዚህ አምራቾች አበባውን ወደ ውጪ ልከው የውጪ ምንዛሬ ማምጣታቸው ጥሩ ነገር ቢሆንም አበቦችን በማምረት ሂደቱ የሚጠቀሙባቸው ኬሚካሎች ከፍተኛ የአካባቢ ብክለትን የሚያስከትሉ መሆናቸው በልዩ ልዩ ምሁራን ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ እነዚህ ኬሚካሎች በመሬት ውስጥ የሚኖሩ ጠቃሚ ነፍሳትን (micro organisms) ይገድላሉ ይባላል፡፡ የውሃ ዑደትንም እንደሚያዛቡ ይነገራል፡፡ በትነት መልክ እየቦነኑ አየሩን እንደሚበክሉም በሰፊው ሲጻፍ ቆይቷል፡፡ በዚህም የተነሳ በአበቦቹ ማሳ ዙሪያ የሚኖረው አራሽ ማህበረሰብ ጤናማ የምግብ ስርዓት እንደማይኖረው ተገልጿል (አንዳንዶቹ  ኩባኒያዎች በአካባቢ ላይ ሲያደርሱት በነበረው ጉዳት ምክንያት ከኬኒያና ከኡጋንዳ ተባረው መምጣታቸው በሰፊው ሲጻፍ የቆየ ጉዳይ ነው)፡፡
   ታዲያ “ዶ/ር ተወልደ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣና ዳይሬክተር ሆነው እነዚህ ሀገር አጥፊ ኩባኒያዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዲገቡ እንዴት ፈቀዱ? ” የሚለው የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች “ዶ/ር ተወልደ በሌሎች መድረኮች ሲያሰሙት የነበረውን ድምጽ በነዚህ ኩባኒያዎችም ላይ ማሰማት ነበረባቸው” ባይ ናቸው፡፡ ይሁንና ዶ/ር ተወልደ በአንድ ወቅት በጉዳዩ ዙሪያ ከሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ ነገሩን በቸልታ እንዳላለፉትና ኩባኒያዎቹን መቆጣጠሩ ከስልጣናቸው በላይ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ እርሳቸውን ከሾመው መንግሥት ጋር ልዩነት እንደነበራቸውም አስታውቀዋል፡፡ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የኬሚካሎቹን አጥፊነት ከመናገር እንዳልተቆጠቡም ተናግረዋል፡፡
——
ዶ/ር ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሄር የታዋቂው ደራሲ የስብሐት ገብረእግዚአብሄር ታናሽ ወንድም ሲሆኑ ባለቤታቸው ደግሞ እንግሊዛዊት ናት፡፡ በፌስቡክ የምናውቃት ገጣሚ ሮማን ተወልደም የርሳቸው ልጅ ናት፡፡ ጋሼ ስብሐት “ማስታወሻ” የሚል ርዕስ ባለው የዘነበ ወላ መፅሐፍ “ከተወልደ የሰማሁት ተረት ነው” ብሎ የገለጸውን እንጋብዛችሁና እናብቃ፡፡
  በአንዲት የገጠር መንደር ነው፡፡ አንድ ሰውዬ ከሩቅ ቦታ የመጣ የለቅሶ ድምጽ ይሰማል፡፡ ከዚያው ገደማ የመጣ ገበሬ ያይና “አንተዬ! ያቺ ሴትዮ ምን ሆና ነው የምታለቅሰው” በማለት ጠየቀው፡፡ ገበሬውም “እባክህ ተዋት! እርሷ ልጇ ሞታ ነው የምታለቅሰው፤ እኔ አለሁ አይደለም እንዴ ማረሻዬ ጠፍቶብኝ በፍለጋ የምንከራተተው” በማለት ያልጠበቀውን መልስ ሰጠው (ቂቂቂቂቂ… በጣም ነበር የሳቅሁት፤ ጋሽ ስብሐት እንዳለው ይህቺ ተረት ለዶ/ር ተወልደ ማስተር ፒስ ናት)፡፡
——
አፈንዲ ሙተቂ
መስከረም 6/2007
——
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his facebook page. Just click this link



(አፈንዲ ሙተቂ)
——
እነሆ ስለሒሳብና ስለ እውቁ የሒሳብ ጀግና በጥቂቱ ልናወጋችሁ ነው፡፡ ጀግናችን ፎቶግራፍ ከተፈጠረበት ዘመን አስቀድሞ የኖረ በመሆኑ ፎቶውን ልናሳያችሁ አንችልም መቼስ!…. በምስሉ ላይ የምትመለከቱት የሒሳቡ ጀግና የተወለደበት 1200ኛ ዓመት ሲከበር ታላቋ የሶቪየት ህብረት ያሳተመችውን  የመታሰቢያ ቴምበር ነው፡፡ ሰውየውን ከሶቪየቶች ጋራ ምን አገናኘው? ከወደታች እንመጣበታለን፡፡ አሁን ወጋችንን በመሰረታዊ ጉዳዮች እንጀምር፡፡
          *****
  እስቲ ከዜሮ ጀምሩና በቅደም ተከተል የሚመጡትን ቁጥሮች ጻፉ፡፡ 1፣ 2፣ 3፣ ….. አስር ስትደርሱ ሌላ ቁጥር ለማግኘት አትችሉም አይደል?… አዎን! አስር ለማለት ከፈለጋችሁ አንድና ዜሮን ጎን ለጎን በማድረግ ትጽፋላችሁ፡፡ ሌሎቹንም ቁጥሮች ለመጻፍ ከፈለጋችሁ በነዚህ ቁጥሮች ትጠቀማላችሁ፡፡
   በጥንት ዘመን ግን እንዲህ ዓይነት ነገር አልነበረም፡፡ የጥንት ግብጻዊያን ይገለገሉበት በነበረው የሄሮግሊፍ (hieroglyphic) አጻጻፍ ሁሉንም ነገር በተለየ ምስል ስለሚመስሉ የሚጠቀሙባቸው ቁጥሮች ብዛትም ማለቂያ አልነበረውም፡፡ ሮማዊያን በበኩላቸው ፊደልን እንደ ቁጥር ሲጠቀሙ ነው የኖሩት፡፡ ይህኛው የቁጥር ዘዴም ወጥ የሆነ ቀመር ስለሌለው ትልልቅ ቁጥሮችን ለመጻፍ ይቅርና በመቶና በአንድ ሺህ መካከል ያሉ ቁጥሮችን እንኳ ሳይደናግሩ ሊጽፉበት ይከብዳል፡፡ በሌሎች የዓለም ክፍሎች ያሉ የቁጥር ዘዴዎችም (numeration systems) ተመሳሳይ ጉድለቶች አሏቸው፡፡ በመሆኑም ከጭንቀት ለመገላገል የሚፈልግ ሰው በመግቢያዬ ወደጠቀስኩት የአቆጣጠር ዘዴ መመለሱ የግድ ነው፡፡
  ይህ ዘዴ “የሂንዱ-ዐረብ የቁጥር ዘዴ” (Indo-Arabic Numeration System) ይባላል:: ከስያሜው እንደምትረዱት “ህንድ”ና “ዐረቢያ” በጋራ በመሆን ለዓለም ህዝብ ያበረከቱት ታላቅ ገጸ-በረከት ነው፡፡ የቁጥሮቹ መሰረት የሆኑት ምልክቶች የተወጠኑት ከክርስቶት ልደት በፊት በሀገረ-ህንድ ነው፡፡ እነዚያ ምልክቶችም 1-እስከ 9 ያሉትን ቁጥሮች ብቻ የሚወክሉ ነበሩ፡፡ ከክርስቶስ ልደት በኋላ በመጀመሪያው ምእተ- ዓመት ምልክቶቹ ከህንድ ተሻግረው ወደ ፋርስ፣ ግብጽ፣ ሜሶጶጣሚያ፣ ሶሪያና ዐረቢያ ገቡ፡፡ በነዚህ ሀገራት የሂሳብ ሊቃውንትና በነጋዴዎች እጅ ሲሸከረከሩም ቆዩ፡፡ በ800 ዓ.ል. ገደማ ግን አንድ ሰው ከባግዳድ ተነሳና ምልክቶቹን በማሻሻል አሁን ያሉትን ቁጥሮች አስገኘ፡፡
 ታዲያ ይህ ሰው ቁጥሮችን በማስገኘቱ ብቻ አላበቃም፡፡ ከዚያ በፊት የማይታወቁ የሂሳብ ጽንሰ-ሐሳቦችንም ለዓለም አስተዋውቋል፡፡ ከነዚያ ጽንሰ-ሐሳቦች መካከል የመጀመሪያው “the concept of Zero” ይባላል፡፡ ሰውዬው ዘጠኙ ቁጥሮች በትክክል ሊሰሩ የሚችሉት ዜሮ ከታከለችባቸው ብቻ መሆኑ ገብቶታል፡፡ በዚህም መሰረት ዜሮን በራሱ በመፈልሰፍ በአስሩ ቁጥሮች ሁሉንም ዐይነት “ህልቅ” (number) ለመጻፍ እንደሚቻል አሳይቷል፡፡ በተጨማሪም በቁጥሮቹ በትክክል ለመጠቀም ከተፈለገ የሂሳቡ ዓምድ “አስር” (base ten) መሆን እንዳለበት አስገንዘቧል (ከዚያ በፊት ሂሳቡ ወጥ ዓምድ አልነበረውም፡፡ ግሪኮች አስራ ሁለትን ወይንም “ደርዘን”ን ነበር እንደ ዓምድ የሚጠቀሙት፡፡ ለባቢሎኒያ እና ለአሶሪያ ሰዎች ደግሞ የሂሳቡ ዓምድ “ስድሳ” ቁጥር ነበረ)፡፡
          *****
ለጥንት ሰዎች ሂሳብ ማለት ሁለት ነገር ነው፡፡ አንደኛው በየቀኑ ነገሮችንና የምንደምርበት፣ የምንቀንስበት፣ የምናባዛበትና የምንቀንስበት መሰረታዊው የሂሳብ ዘርፍ ነው፡፡ ይህም “አርቲሜቲክ” ይባላል፡፡ ሌላኛው ደግሞ ስፋት፣ ርዝመት፣ ወርድ፣ መጠነ ዙሪያ፣ ቁመት ወዘተ የመሳሰሉትን ለመስፈር የምንጠቀምበት “ጂኦሜትሪ” ነው፡፡
 ታዲያ ከላይ የጠቀስነው የባግዳዱ ሰውዬ ከሁለቱ የሂሳብ ዘርፎች ወጣ በማለት መመራመር ጀመረ፡፡ የምርምሩን ውጤትም “ሒሳቡል ጀብር ወል-ሙቃበላ” በሚል ርዕስ አሳተመ፡፡ መጽሐፉ በልዩ ልዩ ምሁራን እጅ ሲገባም ጥንት  ያልነበሩ አዳዲስ የሂሳብ ስልቶችን፣ ስሌቶችንና ዘዴዎችን አጭቆ የያዘ አዲስ የሂሳብ ዘርፍ እንደፈጠረ ታወቀለት፡፡ በመሆኑም አዲሱ የሂሳብ ዘርፍ በመጽሐፉ ስም “ሒሳቡል-ጀብር” በሚል ተሰየመ፡፡ መጽሐፉ ወደ ላቲን ሲተረጎም ደግሞ ስያሜው “አልጄብራ” ተብሎ ተቀየረ፡፡
          *****
ያ የሒሳብ ሊቅ “ሙሐመድ ኢብን ሙሳ” ይባላል፡፡ የተወለደውና አብዛኛውን ዘመኑን ያሳለፈው በአሁኗ የኢራቅ መዲና በባግዳድ ውስጥ ነው፡፡ ይሁንና ወላጆቹ “ኸዋሪዝም” ከምትባለው የመካከለኛው እስያ ክፍለ ሀገር (በኡዝቤኪስታን ውስጥ የምትገኝ) ወደ ባግዳድ የመጡ በመሆናቸው ራሱን ሲጠራ “አል-ኸዋሪዝሚ” በሚል ስም ይጠቀም ነበር፡፡ የዓለም ህዝብም እርሱን የሚያውቀው በዚሁ ስም ነው፡፡ የሒሳብ ሊቃውንት በበኩላቸው ስራዎቹ ዘወትር ይታወሱ ዘንድ “አልጎሪዝም” (algorithm) የተባለውን የስሌት ዘዴ በስሙ ሰይመውለታል፡፡
 አል-ኸዋሪዝሚ በመላው ዓለም የተከበረ ምሁር ነው፡፡ በዓለም ታሪክ ከፍተኛ ተጽእኖ ፈጣሪ ናቸው ከሚባሉት 100 ሳይንቲስቶች መካከልም ስሙ አለ፡፡ በዚህም የተነሳ እርሱ የተወለደባት ኢራቅ፣ ለተወሰነ ጊዜ የኖረባት ኢራን እና ወላጆቹ የተገኙባት ኡዝቤኪስታን “የኔ ነው” በሚል ይወዛገቡበታል፡፡ እንግዲህ የቀድሞዋ ሶቪየት ህብረት በምስሉ ላይ የምትመለከቱትን የመታሰቢያ ቴምብር ያሳተመችው “አል-ኸዋሪዝሚ የኔ ነው” በሚል መነሻ ነው (ኡዝቤኪስታን ከ1924 እስከ 1991 የሶቪየት ህብረት አካል እንደነበረች አስታውሱ)፡፡
  
ቢሆንም አል-ኸዋሪዝሚን የአንድ ሀገር ብሄራዊ ጀግና ብቻ አድርጎ ማየቱ ለዚህ ዘመን ሰው አይስማማም፡፡ ስራው መላውን ዓለም ያዳረሰ በመሆኑ የሁሉም ህዝቦች ብሄራዊ ሀብት ተደርጎ ቢታይ ነው የሚመረጠው፡፡
  —–
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 8/2007
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ                                  
—–
በ7ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ የተጠነሰሰው እስላማዊ ኪነ-ህንጻ በአስራ አራት ክፍለ ዘመናት ውስጥ እያደገ ብዙ ፈርጆች ያሉት የጥበብ  ዘይቤ ሊሆን በቅቷል፡፡ በዓለም ዙሪያ ከፍተኛ አድናቆት የተቸራቸው ቋሚ ግንባታዎችንም አበርክቷል፡፡ በካይሮ ከተማ የሚገኘው የአል-አዝሃር መስጊድ፣ የደማስቆው “የበኑ ኡመያ” መስጊድ (the Omayyad Mosque)፣ የኢስታንቡል “ሱሌይማኒያ” መስጊድ፣ በኢስፋሓን የሚገኘው የኢማም አደባባይና መድረሳ (Midyyan-e-Imami)፣ የህንዱ ታጅማሃል፣ ታላቂ የቁርጡባ መስጊድ (Great Mosque of Cordoba)፣ የግሪናዳ ከተማ መከላከያ ግንብ (fortress) እና ልዩ ልዩ ግንባታዎች፤ የፌዝ ከተማ የመከላከያ ግንብና ጥንታዊው የቃራዊያን መስጊድ (ሞሮኮ)፣ ከጭቃ የተሰሩት የቲምቡክቱ መስጊዶች ወዘተ… ከተደናቂ እስላማዊ ግንባታዎች ጥቂቶች ናቸው፡፡
እስላማዊ ኪነ-ጥበብ ብዙ ፈርጆች እንዲኖሩት ያደረገው በባህሪው “ሆደ ሰፊ” በመሆኑ ነው፡፡ ይህም ሲባል ከሙስሊሙ ዓለም የተገኙት የኪነ-ህንጻ ጠቢባን በየሀገራቸው የነበሩትን ጥንታዊ የንድፍ ዘይቤዎች ከእስልምና መርሆች ጋር በማጣጣም አዳዲስ የኪነ-ህንጻ ዘይቤዎችን ይፈጥሩ ነበር ለማለት ነው፡፡ ለምሳሌ በኢስታንቡል ከተማ የሚገኙት ታላላቅ መስጊዶች የተሰሩት የጥንቱን የቤዛንታይን ኪነ-ህንጻ ከዐረቢያና ከፋርስ ኪነ-ህንጻ ጋር በማዋሃድ በተፈጠረው የቱርክ ኪነ-ህንጻ ዘይቤ ነው፡፡ የቲምቡክቱ መስጊዶችም የማሊን ጥንታዊ የኪነ-ህንጻ ጥበብ መሰረት በማድረግ ነው የተሰሩት፡፡
ጥንት ከተገነቡት እስላማዊ ቅርሶች መካከል ከፊሎቹ ጠፍተዋል፡፡ ግማሽ ያህሉ ግን ዛሬም ቋሚ ሆነው ታሪክን ይመሰክራሉ፡፡ በእስላማዊ ግንባታዎቻቸው በዓለም ዙሪያ የተደነቁት ከተሞች የሚከተሉት ናቸው፡፡
1.      መካ
2.     መዲና
3.     እየሩሳሌም
4.     ባግዳድ (ኢራቅ)
5.     ሰመራ (ኢራቅ)
6.     ቡኻራ (ኡዝቤኪስታን)
7.     ሰመርቀንድ (ኡዝቤኪስታን)
8.     ደማስቆ (ሶሪያ)
9.     ኢስታንቡል (ቱርክ)
10.    ሂራት (አፍጋኒስታን)
11.     መዘር-ኢ-ሸሪፍ (አፍጋኒስታን)
12.    ቁርጡባ (ስፔን)
13.    ግሪናዳ (ስፔን)
14.    ካይሮ (ግብጽ)
15.    ሰንዓ (የመን)
16.    ዘቢድ (የመን)
17.    ፌዝ (ሞሮኮ)
18.    መራኪሽ (ሞሮኮ)
19.    ቱኒስ (ቱኒዚያ)
20.   ቲምቡክቱ (ማሊ)
21.    ጄኔ (ማሊ)
22.   ሀረር (ኢትዮጵያ)
23.   ዛንዚባር (ታንዛኒያ)
24.   ኒሻፑር (ኢራን)
25.   ኢስፋሓን (ኢራን)
26.   ሺራዝ (ኢራን)
27.   ቴህራን (ኢራን)
28.   ጠብሪዝ (ኢራን)
29.   ዴልሂ (ህንድ)
30.   አግራ (ህንድ)
እስላማዊ ኪነ-ህንጻ ሲጠቀስ በቀዳሚነት ከሚወሱት ጠቢባን መካከል አንዱ ከ1489 እስከ 1588 የኖረው ቱርካዊው “ሲናን” ነው፡፡ ቱርኮች ይህንን ሰው ሲጠሩት “ኮጃ ሚማር ሲናን”፣ ማለትም “ታላቁ አርክቴክት ሲናን” ይሉታል፡፡ ችሎታውን ሲገልጹም “እርሱን የመሰለ የኪነ-ህንጻ ጠቢብ አልተፈጠረም” ነው የሚሉት፡፡ በርግጥም በመቶ የሚቆጠሩ “እጹብ ድንቅ” የተባሉ ስራዎቹን ያየ ሰው በከፊልም ቢሆን የቱርኮችን አባባል መጋራቱ የማይቀር ነው፡፡
 “ሲናን” የተወለደው “አጊርናዝ” በተባለች የቱርክ አነስተኛ ከተማ ነው፡፡ በልጅነቱ በአባቱ ስር የአናጺነትና ድንጋይ የማሳመር ጥበብን ተማረ፡፡ አንድ ቀን ግን ህይወቱን የቀየረ አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ በዚያ ቀን (በ1521) የኦቶማን ቱርክ ወታደራዊ ኦፊሰሮች ወደ ሲናን መንደር ሄደው ለውትድርና የሚቀጠሩ ወጣቶችን ይመዘግቡ ነበር፡፡ የሲናን ወታደራዊ አቋም የሚያመረቃ ሆኖ ስለተገኘ እርሱንም መዘገቡትና ወደ ቁስጥንጥንያ (የአሁኗ ኢስታንቡል) ወሰዱት፡፡ እዚያም ልዩ ልዩ ትምህርቶችን እንዲያጠና አደረጉት፡፡
የሲናን የጥበብ ተሰጥኦ መታየት የጀመረው በ1530 ድልድዮችንና ልዩ ልዩ ወታደራዊ ግንባታዎችን መስራት ሲጀምር ነው፡፡ በ1539 ግን ከውትድርናው ዓለም ተሰናብቶ የሲቪል ግንባታዎችን ጀመረ፡፡ በቀጣዮቹ 40 ዓመታትም ቱርክን በዓለም ዙሪያ ያስጠሯትን የልዩ ልዩ ግንባታዎችን ንድፍ እየወጠነ በራሱ አመራር በማስገንባት ለአግልግሎት አበቃ፡፡
ሲናን በህይወት ዘመኑ 79 መስጊዶችን፣ 34 ቤተ መንግሥቶችን፣ 33 የህዝብ የመታጠቢያ ገንዳዎችን (በተለምዶ “Turkish bath የሚባሉት)፣ 19 የመቃብር ስፍራዎችን፣ 55 ትምህርት ቤቶችን፣ 16 የድኾች መኖሪያ ማዕከላትን፣ 7 የከፍተኛ ደረጃ መድረሳዎችን፣ 12 ታላላቅ ምግብ ቤቶችን ሰርቷል፡፡ የፍሳሽ መውረጃዎች፣ ፋውንቴኖች፣ ሆስፒታሎችና ሌሎችንም ገንብቷል፡፡ የሁሉንም ግንባታዎች ንድፍ (ዲዛይን) የሰራው ራሱ ሲሆን በመሃንዲስነት አስጀምሮ የሚጨርሰውም እርሱ ነበረ፡፡
ከሲናን ግንባታዎች መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት የሱሌይማኒያ መስጊድ (በፎቶው ላይ ያለው)፣ የሻሕ ዛድ መስጊድ እና የሰሊም መስጊድ ናቸው (የመጀመሪያዎቹ ሁለቱ በኢስታንቡል ነው የሚገኙት፤ የሰሊም መስጊድ ግን በኢድሪን ከተማ ነው የተሰራው)፡፡ ሲናን የኔ ምርጥ ስራ ነው የሚለው “የሻህ ዛድ መስጊድ”ን ነው፡፡ የኪነ-ህንጻ ጠበብት በጣም የሚያደንቁት ግን የሱለይማኒያ መስጊድን ነው፡፡
—-
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 6/2007
—-
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
በህይወት እስካለን ድረስ ተረት መተረታችንን አናቆምም፡፡ እነሆ ለዛሬም በምሥራቁ የሀገራችን ክፍል እየተደጋገሙ የሚነገሩ ሁለት ትራጄዲ ተረቶችን አዘጋጅተንላችኋል፡፡
===የተንኮል ገበቴ===
እናት አንድ ልጅ ብቻ ነበራት፡፡ ይህንንም ልጅ በብዙ ልፋት ካሳደገችው በኋላ ለአቅመ አዳም ሲደርስ ዳረችው፡፡ ታዲያ የልጁ ሚስት እናትዬውን የምትወድ አልነበረችም፡፡ በብዙ አድራጎቷ ትበድላታለች፡፡ ይብስ ብሎ ደግሞ እናትየዋ ታወረች፡፡ ሚስትም በደሏን አጠናከረች፡፡ በተለይም ሴትዮዋን በጣም የምትበድለው ለእናትዮዋ በምታቀርበው ምግብ ነው፡፡
 ለምሳሌ ለእራት ገንፎ ስታቀርብላት ባሏም ሆነ ሌላ ሰው ዐይኑን እንዳይጥልበት በገንፎው ላይ ቅቤ ትጨምርበታለች፡፡ ነገር ግን ቅቤው ወደ መሬት እንዲፈስ ገንፎው የሚቀርብበትን ገበቴ በአንድ በኩል በስታዋለች፡፡ ልጁ እናቱ ገንፎ በቅቤ የበላች ስለሚመስለው ሚስቱን አይናገራትም፡፡ ሆኖም ገንፎው ቀስ እያለ ወደ መሬት ስለሚፈስ እናትዮዋ አታገኘውም (እናትዮዋ ዐይነስውር መሆኗን አስታውሱ)፡፡
ዘመን አለፈ፡፡ የልጁ እናትም አረፈች፡፡ ልጅየውም ካገባት ሚስቱ አንድ ልጅ ወልዶ ሞተ፡፡ የትናንትናዋ ሚስት የአዲሱ ልጅ እናት ሆነችና ከልጇ ጋር መኖር ጀመረች፡፡ ልጇ ለአቅመ አዳም ሲደርስ እርሷም በተራዋ ከአንዲት ወጣት ጋር በጋብቻ እንዲጣመር አደረገችው፡፡ ሶስቱ ሰዎች በአንድ ላይ መኖር ጀመሩ፡፡ እናት ስታረጅ እንደ ትልቋ እናት (የሞተችው የቧላ እናት) ታወረች፡፡ አንድ ቀን ምግብ ሲቀርብላት ገንፎው ቅቤ የሌለው ሆነባት፡፡ ወዲያውኑ የሆነ ነገር ትዝ አላትና ገበቴውን መዳበስ ጀመረች፡፡ በርግጥም እንደጠረጠረችው ገበቴው በአንድ በኩል የተበሳ ሆኖ አገኘችው፡፡ እናም ድሮ ስትፈጽመው የነበረውን በደል በማስታወስ ከልቧ አዘነች፡፡ እንዲህም አለች፡፡
“አይ ገበቴ! አይ ገበቴዋ! ከምኔው ዞረሽ ወደኔ መጣሽ?!! ግድ የለም፡፡ የእጄን ነው ያገኘሁት፡፡ ያኔ የባሌን እናት ባልበድል ኖሮ ዛሬ ምግቤ እኔ በቀደድኩት ገበቴ ባልተሰጠኝ ነበር”
የሴትዮዋ ንግግር ከልጁ ሚስት ጆሮ ጥልቅ አለ፡፡ እናም ሚስት በሰማችው ነገር ሽምቅቅ አለች፡፡ “ለካስ የኔም የወደፊት እጣ በዚህች ገበቴ መብላት ነው?” እያለች አሰላሰለች፡፡ ወዲያውኑ የባሏን እናት ይቅርታ ጠይቃ ያቺን የተንኮል ገበቴ እንክትክት አድርጋ ሰባበረቻት፡፡ እናትም ምግባቸው በጤነኛ ገበቴ ይቀርብላቸው ጀመር፡፡
===ሁለቱ አባቶችና ሁለቱ ልጆች===
ልጅና አባት አብረው ይኖሩ ነበር፡፡ አባት ልጁ ትዳር እንዲይዝ ካደረገው በኋላ ሁሉንም ነገር አስረከበው፡፡ ለራሱም ጡረተኛ ሆኖ ከልጁ ቤት ጀርባ ከነበረች አንዲት አነስተኛ ጎጆ መኖር ጀመረ፡፡ ይሁንና አባትዬው በጸባዩ ነጭናጫ ነው፡፡ በተለይ ልጅ ለስራ ወደሌላ ቦታ በሚሄድበት ጊዜ የልጁን ሚስት በሆነ ባልሆነው ይነዘንዛታል፡፡ ሚስትም በንጭንጩ ተማረረችና ባሏ ሲመጣ “ወይ አባትህን ከዚህ ቤት አርቅልኝ፤ ወይ ደግሞ ፍታኝ” አለችው፡፡
ልጁ ወደ አባቱ ሄደና “አባቴ! እዚህ ቤት ስትኖር አፍህን ዝጋልኝ!! ካልሆነ ግን ወደ ገደል እወረውርሃለው” በማለት አስጠነቀቀው፡፡ አባትም “አረ አትወርውረኝ! ከእንግዲህ አፌን እይዛለሁ” በማለት ተማፀነው፡፡ በመሆኑም አባት ከነርሱ ጋር መኖሩን ቀጠለ፡፡ ነገር ግን አባት ቃሉን ሊያከብር አልቻለም፡፡ ልጁ ከቤት እስኪወጣ ጠብቆ ሚስትዬውን ይጨቀጭቃት ገባ፡፡ በዚህ የተናደደችው ሚስት ወደ ባሏ ሄዳ “ነገ አባትህን ከዚህ ቤት ካላስወጣህልኝ እሄድልሃለሁ” አለችው፡፡ ባልም “ግድ የለም! ነገ ገደል ውስጥ እጥለዋለሁ” አላት፡፡
በንጋቱ ልጅየው ሽማግሌ አባቱን ወደ ገደል ሊወረውረው ተነሳ፡፡ ከገደሉ ጫፍ ላይ ካደረሰው በኋላም “አባቴ! ብትፈልግ ገደል ግባ! ብትፈልግ የፈለግከውን ሁን፡፡ አባቴ ስለሆንክ ግን በራሴ እጅ አልወረውርህም፡፡ ትዳሬንም እወዳለሁና ከቤቴ እንድትመለስ አልፈቅድልህም” አለው፡፡ አባትየውንም እዚያው ትቶት ሄደ፡፡
ዘመን አለፈ፡፡ የድሮው ልጅ በተራው አባት ሆነ፡፡ ልጁም አገባ፡፡ አባትም ከልጁ ጋር መኖር ጀመረ፡፡ ታዲያ እርጅና ሲመጣ ይህኛውም  አባት ልክ እንደ ድሮው አባት ጨቅጫቃ ሆነ፡፡ የልጁን ሚስት በረባ ባልረባው ይጨቀጭቃት ጀመር፡፡ ልጁም ጭቅጭቁ ሲሰለቸው አባትዬውን ወደ ገደል ሊወረውረው ተሸክሞት ተነሳ፡፡ ረጅም ርቀት ከተጓዙ በኋላ የታዘለው አባት ልጁን እንዲህ አለው፡፡
  “እዚሁ ጋ ብትተወኝ ይሻለኛል፤ እኔም ያኔ አባቴን ከዚህ አላሳለፍኩትም”፡፡
*****
  አያድርስ ነው ወገን! “ሁሉም የዘራውን ነው የሚያጭደው” የሚለው ምሳሌ አሁን ላይ የማይሰራ ቢመስልም ጊዜው ሲደርስ እውነት መሆኑ አይቀርም፡፡ አላህ ከእንዲህ ዓይነት ክፋት ይጠብቀን፡፡
በነገራችን ላይ የመጀመሪያውን ተረት የነገሩን ጎረቤቴ የነበሩት “ሀቦ ኑሪያ” ናቸው፡፡ ሁለተኛውን ተረት የአባቴ የቅርብ የስጋ ዘመድ ከሆኑት ሼኽ ሙሐመድ ሑሴን ቲርሞ የሰማሁት ነው (በኋላ ላይ ስብሐት ገብረእግዚአብሄር ጽፎት ባነበውም ተረቱን በቅድሚያ የሰማሁት ከሼኽ ሑሴን አንደበት ነው)፡፡
——
አፈንዲ ሙተቂ
ግንቦት 26/2006
አዳማ!!
—–
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links

በህይወት እያሉ ተረት ለመሆን የበቁትና በጎጃም ክፍለ ሀገር የደብረ ወርቅ ወረዳ አስተዳዳሪ የነበሩት አቶ “ቆምጫ አምባው” በዚህ ፎቶግራፍ የምትመለከቷቸው ሰውዬ ናቸው፡፡ አቶ ቆምጬ በአሁኑ ወቅት በትውልድ ከተማቸው በጥብቅና ሙያ ላይ ተሰማርተዋል፡፡ (ፎቶ፡ ዘ-ኢትዮጵያ ጋዜጣ)

Image



(አፈንዲ ሙተቂ)
—-
   በምስሉ ላይ ያለውን ሰውዬ ታውቁታላችሁ አይደል?… ህንዳዊ የሲኒማ አክተር ነው፡፡ በትክክለኛ ስሙ “ሚቱን ቻክራቦርቲ” ይባላል፡፡ የሀገራችን የሲኒማ አፍቃሪዎች ግን “Disco Dancer” በሚባለው ፊልም ውስጥ በሚጠራበት ስሙ ነው የሚጠሩት፡፡

አዎን! “ጂሚ” ነው፡፡ ያ “እኔ እኮ የዲስኮ ዳንሰኛ ነኝ” እያለ የሚሞላቀቀው ጆሊ!!
  I am a disco dancer
 ዘንደኪ ሜራሃና!
 ሜንዲሽቲ ከቲቫና
ኮቹሞ ሀነቾ
ሀ ሜሪ ሰቲ ነቾ
 
  አዎን!!  እርሱ እኮ ነው፡፡ (ዲስኮ ዳንሰርን በዚህ ሊንክ ላይ ተመልከቱት https://www.youtube.com/watch?v=7JdEZoffm-Q   )
 “ጂሚ ጂሚ ጂሚ… አጃ.. አጃ” እያለች የምታለቅስለትን ልጅስ አስታወሳችኋት?… ወይ ስታዝን!… ጂሚ በኤሌክትሪክ ጊታር ተቃጥላ የሞተችበት የእናቱ ሐዘን ቅስሙን ሰብሮት ሙዚቃውን እርግፍ አድርጎ ስለተወ ሽልማቱን ሊያጣ ደርሶ ነበር፡፡ በመሆኑም ነው ልጅቷ  “ጂሚ.. ጂሚ.. አጃ.. አጃ.” እያለች የተለማመጠችው፡፡
በልጅነታችን Disco Dancer የሚባለውን ፊልም ሳናየው በፊት በቪዲዮው ውስጥ ያሉት ዘፈኖች የተሰበሰቡበት ካሴት በጣም ተወዳጅ ሆኖ ነበር፡፡ በመሆኑም በሰርግ ቤትም ሆነ በወላጆች ቀን በዓል ቀዳሚ ምርጫ ሆኖ ይከፈት የነበረው እርሱ ነው፡፡ እርሱ በደንብ ከተደመጠ በኋላ ነው የማይክል ጃክሰን “ትሪለር” በሁለተኛ ደረጃ የሚከፈተው (በሶስተኛ ደረጃ የ“ቦኒ ኤም” ዳዲ ኩል ነው የሚመረጠው)፡፡
   ታዲያ ዕድላችን ተቃንቶ የህንድ ሲኒማ በ1978 ወደ ከተማችን ሲመጣ ጂሚን በውኑ ያየነውን ያህል ነው የፈነጠዝነው፡፡ ጂሚን የማየት የዘመናት ጥማታችንን የተወጣንበት የመጀመሪያው ፊልም  “Jimmy and His Elephant” የሚል ርዕስ የነበረው ይመስለኛል (በአማርኛ “እኔና ዝሆኔ” ይሉት ነበር)፡፡ በርግጥም ጂሚ በፊልሙ ውስጥ ከዝሆን ጋር ጉደኛ ዳንስ ይደንሳል፡፡ ዝሆኑ እንደ ጥሩምቦንና እንደ ሳክስፎን “ፓፓፓ” እያለ ድምጽ አውጥቶ ይሞዝቃል፡፡
    ከሁለት ዓመት በኋላ (በ1980) ጂሚ በጣም የታወቀበት `Disco Dancer”  መጣ፡፡ ማን ይቻለን!! አቤት ፌሽታ!! የፊልሙ ፖስተር (በያኔው አጠራር “ሌክራም”) በከተማችን ማዕከላዊ ስፍራ ላይ በነበረው የአቶ ዋጋዬ ይደነቃል ሱቅ ግድግዳ ላይ ሲለጠፍ እርሱን ለማየት የነበረው ግርግር እስከ አሁን ድረስ ይታወሰኛል፡፡ ማታ በ12፡00 ሰዓት ለሚታየው ፊልም ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ነው የተሰለፍነው፡፡
   ፊልሙ ተጀመረ፡፡ ጂሚ በልጅነቱ Goron Ki Na kalon Ki እያለ ከሚዘፍነው ዘፈኑ ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ ልባችን እየተሰቀለ አየነው፡፡ በርሱ ዳንስና እናቱን በገደለበት ተንኮለኛ ሙጅሪም (በኛ አጠራር “ፋሩቅ” የሚባል)መሀል እየተወዛወዝን አጣጣምነው፡፡ ፊልሙን ባየንበት ማግስት ወሬው እርሱ ብቻ ሆነ፡፡ በየሆቴሉ፣ በየሻይ ቤቱና በየጥናት ቤቱ የጂሚ ፖስተሮች ተለጠፉ!!
—-
በ1981 ደግሞ ጂሚ ሌላ ተአምር ይዞ መጣ፡፡ Kassam Paida Karne Wale Ki (በአጭር አጠራር Kassam Paida) የሚባል ፊልም ውስጥ ያየነው ጂሚ ድሮ ከምናውቀው ጂሚ በእጥፍ ጨመረ፡፡ ይህኛው ጂሚ በሙዚቃው ብቻ ሳይሆን በአለባበሱም ከሌላ ፕላኔት የመጣ መልአክ መስሎ ነው የታየን፡፡ በዳንሱና በአለባበሱ በጣም ስላፈዘዘን “ከጂሚና ከማይክል ጃክሰን ማን ነው የሚበልጠው?” የሚል ውርርድም ተጀምሮ ነበር (በነገራችን ላይ Kassam Paida የሚባለው ፊልም በአማርኛ “ጂሚ እንደ ማይክል” ተብሎ ነው የሚጠራው፤ በፊልሙ ውስጥ ጂሚ የሚዘፍነው አንዱ ዘፈን ዜማው ከማይክል ዘፈን ስለተኮረጀ ይመስለኛል እንደዚያ የተባለው፤ ደግሞም ማይክል Thriller በተሰኘው ዘፈን እንዳደረገው ሁሉ ጂሚም ሙታንን ከመቃብር አስነስቶ አስደንሷል)፡፡
   ከሁሉም በላይ Kassam Paida ውስጥ የተወነው ጂሚ በጣም ያስደነቀን  በድራም አመታቱ ነው፡፡ በፊልሙ ውስጥ አብራው የተወነችው Salma Agha የተባለች ፓኪስታናዊት አክትረስ ናት፡፡ ይህቺ አክትረስ Joom Joom Joom Ba Bah እያለች የምትጫወተው ዘፈን አለ፡፡ በዚያ ዘፈን ላይ በሙዚቃ መሳሪያ ካጀቧት ሙዚቀኞች መካከል አንዱ ጂሚ ነው፡፡ ጂሚ ድራሙን ሲያተረማምሰው አፍ ያስከፍታል፡፡ በተለይም አንድ ቦታ ላይ “ሳልማ” (በፊልሙ ውስጥ የምትጠራበት ስም “ኒና” ነው) ዘፈኑን እያስኬደችው ታቆመውና ወደ ጂሚ ዞራ የዐይን ምልክት ትሰጠዋለች፡፡ ይሄኔ ጂሚ ድራሙን ይቀውጠዋል፤ እያርበደበደ ያንቀጠቅጠዋል፡፡ ዲም..ዲም ዲም.. ዲም….ተራራም.. ዲም…..ዳም ዳም…ኪሽ…ኪሽ…..!!  እንዲያው እኮ በኤሌክትሪክ የሚሰራ ማሽን ነው የሚመስለው!!
 
  ጂሚ ድራሙን እንደዚያ አተረማምሶ ሲወቃው በአዳራሹ የነበረው የከተማችን የሲኒማ ተመልካች በሙሉ ከመቀመጫው ተነስቶ በጭብጨባ አድናቆቱን ገልጾለታል፡፡ በሌሎች ከተሞችም ተመሳሳይ ነገር እንደተከሰተ ተነግሮኛል፡፡
 (ያንን የድራም ምት ለማየት ካሻችሁ ይህንን የዩቲዩብ ቪዲዮ ተመልከቱ፡፡ http://www.youtube.com/watch?v=IFjKnIgd9js  )
——-
“ጉድና ጅራት በስተመጨረሻ ነው” አሉ!! ሰሞኑን የሆነ ነገር ፈልጌ You Tubeን ስጎረጉር የጂሚን የቆዩ ቪዲዮዎች አገኘሁ፡፡ ያኔ በልጅነታችን ሲያስጨበጭቡን የነበሩት የዲስኮ ዳንሰር እና የKassam Paida ዘፈኖች በመደዳ ተደርድረዋል፡፡ “ወይ ጂሚ! ከየት ተገኘህ ደግሞ” አልኩኝና አንድ ሁለቱን ከፍቼ አየኋቸው፡፡ ጂሚ አሁን ያለበትንም ሁኔታ የማወቅ ጉጉት ስላደረብኝ ኢንተርኔቱን የበለጠ ጎረጎርኩት!!
መቼም ይህ ኢንተርኔት የሚባለው “የሸይጣን ድር” አቃጣሪም አይደል? የአሁኑን ጂሚ ብቻ ሳይሆን የያኔውን ጂሚ ጭምር ቁልጭ አድርጎ አሳየኝ፡፡ “ዳንሱም የውሸት፣ ሙዚቃውም የውሸት፣ ዘፈኑም የውሸት ነው፤ ጂሚ ሌላ ሰው በዘፈነው ሙዚቃ ነው እንደዚያ ሲያጭበረብራችሁ የነበረው”- ይላል ኢንተርኔቱ!!
ይገርማል!! ከዚህ በፊት “የህንድ ፊልም የእውነት ነው” ስንል እንደነበር ጽፌአለሁ፡፡ በሂደትም በፊልም ውስጥ የውሸትና የእውነት ትዕይንቶች ተቀላቅለው እንደሚቀናበሩ ማወቃችንንም ነግሬአችኋለሁ፡፡ በመሆኑም የህንድ ፊልምም የውሸትና የእውነት ቅንብር ነው ብዬ ነበር የማምነው፡፡ አሁን ግን ሁሉም ነገር የውሸት ሆኖ ቁጭ አለ! አይ እዳ!!
    ይህ ጂሚ አናደደኝ !! የምሬን ነው በጣም ነው ያቃጠለኝ!! በውሸት ምት እነ ሳምሶን መላጣን ከጣሪያ ወደ መሬት እያንከባለለ ሲያጭበረብረን የነበረው ሳያንሰው በውሸት ዘፈንና ዳንስ ያታልለናል እንዴ?!! አሁን ያቺ ምትሃተኛ ድራም የውሸት ናት?… በውሸት ነው እንደዚያ ከሳልማ ጋር እየተቀባበሉ “በዘበዛ” ሲያደርጉን የከረሙት?… እኛስ አስመሳዩን ሰውዬ ነው ከማይክል ጃክሰን ስናስበልጠው የነበረው?…
ይገርማል!! የሆሊውድ አክተሮችም በሙዚቀኛና በሙዚቀኛነት ህይወት ላይ ያተኮረ ፊልም ይሰራሉ፡፡ ነገፍ ግን ምዕራባዊያኑ በፊልም ውስጥ የሚዘፍኑት ዘፈንና የሚደንሱት ዳንስ በአብዛኛው የእውነት ነው (ለምሳሌ ጆን ትራ ቮልታን መጥቀስ እንችላለን)፡፡ ጂሚ ሆዬ በውሸት ዘፈንና በውሸት የሙዚቃ መሳሪያ አጨዋወት ስልት ሲያስለፈልፈን ከረመ!! ይኼ ቦንባ!! ይሄ ጉረኛ!!
—-
ደግነቱ እኛ ብቻ አልነበርንም፡፡ “ጂሚ” በመካከለኛው ምስራቅ፣ በምስራቅ አውሮጳ ሀገራትና በሶቪየት ህብረትም ጭምር ነው ዝነኛ የሆነው፡፡( በዚያ ዘመን ከሆሊውድ የመጣ ፊልም በሶቪየት ህብረት አይታይም፤ የህንድ ፊልሞች ግን ይፈቀዳሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ የህንድ ፊልሞች እንደ አሜሪካ ፊልሞች ሶቪየት ህብረትንና የሶሻሊዝም ስርዓትን ስለማያጥላሉና ስለማይተነኩሱ ነው)፡፡  በመሆኑም የኛ መሸወድ የተለየ የሚሆንበት ምክንያት የለም፡፡ ያ እንደዚያ ስናጨበጭብለት የነበረው ጂሚ እኛ ምኑንም ባላወቅነበት ወቅት በካሜራ ጥበብ ቢያታልለንም ዛሬም እናደንቀዋለን!!
ከመልከ መልካሙ ጂሚ ጋር ወደፊት!!
—-
ጳጉሜ 5/2006


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–

በጎንደር የነገሡት የኢትዮጵያ ነገሥታት በታሪካዊ ሚናቸው በእኩል ሚዛን ላይ አይቀመጡም፡፡ አንዳንዶቹ በሰሩት ስራ ስማቸው ዘመንን ተሻግሮ ይዘከራል፡፡ አንዳንዶቹ ግን ስልጣን አልባ ሆነው በስም ብቻ “ንጉሥ” እየተባሉ ይጠሩ ነበር፡፡ የሁላቸውንም ታሪክ መዘርዘር የኛ ዓላማ ባለመሆኑ እርሱን ለታሪክ መጻሕፍት እንተወው፡፡ ለበረካ ያህል ግን ሁለት ነገሥታትን በትንሹ እናውሳቸው፡፡
===ተረት መሳዩ ንጉሥ===
ከስሙ ጀምሮ ሁለመናው ይገርማል፡፡ ታሪኩ እንደ ተረት ያስደምማል፡፡ አንዳንዴ የሚሰራቸው ነገሮች ደግሞ ከባግዳዱ ኸሊፋ ሀሩን አል-ረሺድ ጋር ያመሳስሉታል፡፡
ይህ ንጉሥ “ባካፋ” ይባላል፡፡ አጼ ባካፋ የነገሠው በአድማ ነው፡፡ አጼ ዳዊት ሳልሳዊ በሚባለው ወንድሙ ላይ አምጾ ነው ስልጣንን የተቆጣጠረው፡፡ ታዲያ ለአመጽ ሲነሳ መጀመሪያ ላይ በለስ አልቀናውም፡፡ በውጊያ ስለተሸነፈ ራሱን ሸሽጎ ከአንድ ደብር ለመኖር ተገደደ፡፡ በዚያ ደብር እያለም በአንድ መምህር ስር ቅኔና ዜማ መማር ጀመረ፡፡ እያደር ከዚሁ መምህር ጋር ሚስጢረኛ ሆነ፡፡ ታሪኩንም አንድ በአንድ አጫወተው፡፡
  በአንድ ውድቅት ሌሊት እርሱና መምህሩ ለመጸዳዳት ይወጣሉ፡፡ እዚያ እያሉም ባካፋ ለመምህሩ “መሪጌታ! የኔን ነገር እንዴት ነው የሚያዩት?.. ይህንን ወንድሜን አሸንፌ መንገሥ የምችል ይመስልዎታል?” የሚል ጥያቄ አቀረበ፡፡ መምህሩም “የምትነግሥ ይመስለኛል፤ ነገር ግን ጸሎት ማብዛት አለብህ፣ በጸሎት ሀይል የማይቻል የለም፤ ታዲያ ቀኙ ያንተ ሆኖ አልጋውን በወሰድክ ጊዜ እኔን እንዳትረሳኝ” አለው፡፡ ባካፋም በፍጹም ላይረሳው ቃል ገባለት፡፡
   ዓመታት አለፉ፡፡ ባካፋም ወንድሙን ድል አድርጎ ነገሠ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ድሪቶ የለበሰ ባላገር መጥቶ ከቤተ መንግሥቱ ፊት ቆመ፡፡ ዘበኞቹንም እንዲህ የሚል መልዕክት ለባካፋ እንዲያደርሱለት ለመናቸው፡፡
“ታስታውሳለህ ባካፋ የተባባልነውን
እኔ የአብረሃምን አባት ሆኜ አንተ ሚስቱን”
   ዘበኞቹ የባላገሩን ንግግር እንደ እብድ ወሬ ቆጠሩትና ለባካፋ ላለመንገር ለገሙ፡፡ አንዱ “ነቄ” ዘበኛ ግን ሰውዬው ቅኔ የተናገረ ስለመሰለው “ንጉሡ መልዕክቱን መስማት አለባቸው” በማለት ወደ አጼ ባካፋ ሄዶ ተናገረ፡፡ ባካፋም “እንዴ?! የቅኔ መምህሬ ናቸው፤ በቶሎ አስገቡልኝ” በማለት ዘበኞቹን አዘዛቸው፡፡ በዚህ መንገድ ባካፋ ከጥንቱ መሪ ጌታ ጋር ተገናኘ፡፡ ያኔ የገባውንም ቃል ተግባራዊ አደረገ፡፡
  በነገራችን የቅኔውን ሚስጢር አግኝታችሁታል አይደለም?… የአብረሃም አባት “ታራ” ነው፡፡ የአብረሃም ሚስት ደግሞ “ሳራ” ናት፡፡ ስለዚህ መምህሩ ለማስተላለፍ የፈለገው መልዕክት “እኔ ሳራ አንተ ታራ” የሚል ነው፡፡ ይህም ሁለቱ ሰዎች ሲጸዳዱ ያደረጉትን ውይይት የሚያስታውስ ነው፡፡
*****
    በሌላ ጊዜ ደግሞ ባካፋ እንደ ባግዳዱ ኸሊፋ “ሃሩን አል-ረሺድ” ማንነቱን ቀይሮ ሀገሩን ይጎበኝ ነበር፡፡ ከአንድ ምንጭ አጠገብ ሲደርስ አንድ እረኛ ገጠመውና “የዚህ ሀገር ንጉሥ እንዴት ነው?” አለው፡፡ እረኛውም “ጥሩ ነው፤ ተስማምቶናል፤ ሀገሩ ጥጋብ ነው፤ ደሀን አይበድልም” የሚል መልስ ሰጠው፡፡ ይሁንና ባካፋ ሆን ብሎ እረኛውን መተንኮስ ጀመረ፡፡ “ምን ጥጋብ ነው ትላለህ? እንዲህ ዓይነት ግፈኛ ንጉሥ ነግሦም አያውቅ፤ ደሀውንም እንደርሱ የሚበድል የለም” አለው፡፡ እረኛው “ሰውዬ! እኔ አልዋሸሁም፤ ይህንን ነገረኛነትን ተወኝ፤ ምላስህን ያዝልኝ” አለው፡፡ ባካፋ ግን ትንኮሳውን ቀጠለ፡፡ በዚህ ጊዜ እረኛው ሽመሉን መዝዞ “እምቢ ካልከኝ በዚህ ዝም ትላለህ” በማለት ባካፋን እስኪበቃው ድረስ ደበደበው፡፡
     ከሳምንት በኋላ እረኛው ወደ ቤተመንግሥት ተጠራ፡፡ “ለምን” ብሎ ቢጠይቅ መልስ አልተሰጠውም፡፡ በመሆኑም ፍርሃት ወረረው፡፡ “ምን አጥፍቼ ይሆን?” እያለ ተጨነቀ፡፡ እንዲሁ በጭንቀት እንደተወጠረ ቤተመንግሥት ሲደርስ ከሳምንት በፊት የደበደበው ሰውዬ በዙፋን ላይ ቁጭ ብሎ አገኘው፡፡ እረኛው የባሰውኑ ተርበተበተ፡፡ ይሁንና ንጉሡ የፈገግታ ምልክት ሲሰጠው ልቡ መለስ አለችለት፡፡ ንጉሡም እንዲህ አለው፡፡
  “ከሳምንት በፊት ላሳየሁ ሐቀኝነት አንድ መቶ ከብቶችን ተሸልመሃል”
===የቤተመንግሥቱ ጭውውትና ታሪክ ቀያሪው ፋኖ====
አሁን ደግሞ በጎንደር ቤተ-መንግሥት የተደረገ አንድ ጭውውት እንጥቀስላችሁ፡፡
1ኛ ተናጋሪ (እቴጌ መነን)
አረ ለመሆኑ ምን ይሆን አሳቡ
ሸፍቶ የሄደው ከነቤተሰቡ?
*****
2ኛ  ተናጋሪ (ራስ ዓሊ)
ሰውዬው ኩሩ ነው የተነፋ ልቡ
ይዞ ማዋረድ ነው ይበርዳል ጥጋቡ::
*****
3ኛ ተናጋሪ (አንድ መነኩሴ)
ሰውዬው ብርቱ ነው ስሙ የተጠራ
ጎበዝ እኔ ነኝ ባይ ሀይልን የማይፈራ
በዘዴ በትዕግስት ማባበል ይሻላል
በሀይል ብንለው በጣም ያውከናል፡፡
*****
4ኛ (እቴጌ መነን)
እንዲህ ስትሉ ነው ስሙ የገነነው
የፈራነው መስሎት አገር የሚያብጠው
ዘዴ መላ አታብዙ ጦር ይታዘዝና
ቢቻል ከነነፍሱ ይምጣ ይያዝና
እምቢ ካለም ይሙት በገዛ ጥፋቱ
ላንድ ወንበዴ ሽፍታ አይስጋ መንግሥቱ፡፡
*****
  ይህ ጭውውት በ1840ዎቹ በጎንደር ቤተመንግሥት እልፍኝ ከተደረገ ምክክር የተቀነጨበ ነው፡፡ ይህም “ቴዎድሮስ” በተሰኘው የደጃች ግርማቸው ተክለሃዋሪያት መጽሐፍ የመጀመሪያ ገጽ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ በጭውውቱ ውስጥ “ለምን ሸፈተ” ተብሎ እንደ አጀንዳ የቀረበው የያኔው ደጃች ካሳ ሀይሉ ጉዳይ ነው፡፡ በዚያን ወቅት ካሳ ሀይሉ ከተራ ቤተሰብ ተወልዶ በአስገራሚ ሁኔታ የቤተ መንግሥቱ አባል ሆኖ ነበር፡፡ ታሪክ አለው፡፡
  
ደጃች ካሳ በወጣትነቱ ሽፍታ ሆኖ በቋራና በደምቢያ ይዘዋወር ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ ኢትዮጵያዊያን ሱዳንን ከሚቆጣጠሩት የቱርክ/ግብጽ ገዥዎች ጋር የድንበር ላይ ውጊያ ያካሄዱ ነበር፡፡ ታዲያ በአንዱ ውጊያ ላይ የዘመኑ ዋና መስፍን የነበሩት የራስ ዓሊ ልጅ የሆነችው ወይዘሪት ተዋበች ተማረከች፡፡ ይህም ወሬ ለካሳ ጆሮ ደረሰ፡፡ ካሳ በወቅቱ ሽፍታ ቢሆንም የኢትዮጵያዊያን መሸነፍና በምርኮ መጋዝ በጣም አበሳጨው፡፡ በመሆኑም በቱርኮች ላይ ድንገተኛ አደጋ ጥሎ አተረማመሳቸው፡፡
  ካሳ ይህንን ሲያደርግ ተዋበች ምርኮኛ መሆኗ በቁጭት ውስጥ ጥሎአት በመርዝ ጩቤ ሰውነቷን ወግታ ራሷን ለማጥፋት ሙከራ በማድረግ ላይ ነበረች፡፡ ይሁንና ካሳ በቦታው ደርሶ መርዙ ወደ ሰውነቷ ጠልቆ ሳይገባ ከደሟ ውስጥ መጥጦ ተፋው፡፡ በዚህም የተዋበች ህይወት ተረፈች፡፡ ካሳም ተዋበችን በጀርባው አዝሎ ከውጊያው ስፍራ እየሮጠ ወጣ፡፡ ወታደሮቹም በቶሎ እንዲያፈገፍጉ ትዕዛዝ ሰጣቸው፡፡
   ካሳ ነፍሲያዋን ያተረፈላትን ተዋበችን ለአባቷ ለራስ ዓሊ አስረከባት፡፡ ራስ ዓሊም በጀግንነቱ ተደስተው እሷኑ ዳሩለት፡፡ ሽፍትነቱን ትቶ በቤተመንግሥት እንዲኖርም አደረጉት፡፡ ይሁንና የቤተመንግሥቱ ህይወት በነጻነት መኖርን ለለመደው ካሳ የግዞት ያህል ሆነበት፡፡ በዚያ ላይ መኳንንቱ “የኮሶ ሻጭ ልጅ” እያሉ የሚያሳዩት ንቀት በጣም አቃጠለው፡፡ ተዋበችም በባሏ ላይ በሚደርሰው ንቀትና ማሽሟጠጥ በገነች፡፡ እናም በአንድ ውድቅት ላይ “አንተ ካሳ! ጎራዴህን ታጠቅና ተነሳ፤ ምንጊዜም ከጎንህ ነኝ” አለችው፡፡ ካሳም ሸፈተ፡፡
*****
  እንግዲህ ከላይ የቀረበው ጭውውት ካሳ በሸፈተ በማግስቱ የተደረገ ነው፡፡ በዚያ ቀን በተደረገው ምክክር ደጃች ወንድይራድ የካሳን እጅ ይዞ እንዲመጣ ታዘዘ፡፡ ወንድይራድም ከቤተመንግሥቱ ቀርቦ እየጎረነነ ትዕዛዝ መቀበሉን አረጋገጠላቸው፡፡ ይሁንና ከልክ ያለፈው የወንድይራድ ጉራ ያልጣማቸው ራስ ዓሊ “አንተ ወንድይራድ! ካሳ እንደ ሌላው ሽፍታ አይምሰልህ፤ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው አደገኛ ተዋጊ ነው” በማለት ምክር ቢጤ ቢወርውሩለት ዳጃች ወንድይራድ እንዲህ የሚል የንቀት መልስ ሰጣቸው፡፡
አይስሙ ጌታዬ ሰው የሚለውን
አያስፈራም ካሳ ይንዛ ጉራውን፡፡
ገና መጣ ሲሉት አገር ጥሎ ይሸሻል
ወይንም ካንዱ ደብር ገብቶ ይደውላል፡፡
እንኳን አንድ ሽፍታ ቀማኛ ወንበዴ
ብዙ እመልሳለሁ በጦር በጎራዴ፡፡
እኔ ነኝ ወንድይራድ ታማኝ አሽከርሽ
ያን የኮሶ ሻጭ ልጅ የምቀጣልሽ፡፡
    የወንድይራድ ፉከራና ድንፋታ ከካሳ ጆሮ ገባ፡፡ ካሳም “እናቴን እንዲህ የሰደበውን ባለጌ ባላሳየው እኔ ካሳ አይደለሁም” በማለት መሃላውን አስቀመጠ፡፡ ሁለቱ ሀይሎች ተገናኙ፡፡ ውጊያው ገና ከመጀመሩ የወንድይራድ ፉከራ የአሸዋ ላይ ቤት ሆኖ ፈረሰ፡፡ እቴጌ መነን (የራስ ዓሊ እናት) የተመኩበት ዳጃች ወንድይራድም ተማረከ፡፡ ካሳም መሃላውን ተግባራዊ አደረገ፡፡ ወንድይራድን ቀንና ማታ ኮሶ እያጠጣው ገደለው፡፡
   ከዚያ በኋላ ካሳ በሀገሩ ላይ ገነነ፡፡ ማን ይቻለው እንግዲህ? ደጃች ውቤም ሆኑ ራስ ዓሊ፣ ደጃች ተድላ ጓሉም ሆኑ ደጃች ጎሹ ሁሉም ተራ በተራ ተሸነፉ፡፡ ካሳን ያሸንፋሉ ተብለው የተጠበቁት እቴጌ መነንም በናቁት አማቻቸው እጅ ምርኮኛ ሆነው ወደቁ፡፡ የጥንቱ የቋራ ሽፍታም “ዳግማዊ ቴዎድሮስ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ” ተብሎ ነገሠ፡፡ ንጉሥ ለስሙ ብቻ ቤተመንግሥት የሚቀመጥበት ዘመነ መሳፍንትም አበቃ፡፡ ኢትዮጵያም አዲስ ታሪካዊ ጉዞዋን ተያያዘችው፡፡
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ግንቦት 23/2007
አዳማ
——
(ማስታወሻ፡ ይህ ጽሑፍ ከቀጣዩ መጽሐፌ የተቀነጨበ ነው፡፡ ጽሑፉን በኢንተርኔት ማውጣት ቢቻልም በየትኛውም የህትመት ሚዲያ ማተም ክልክል ነው)
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
የጥንት ግብጻዊያን አንድ ልማድ ነበራቸው፡፡ በየዓመቱ ቆንጆ ልጃገረድ ይመርጡና ለአባይ ወንዝ (ኒል/ናይል) ይሰውለት ነበረ፡፡ እነዚያ ግብጻዊያን ናይል በየዓመቱ መስዋዕቱን ካላገኘ ውሃውን ይቋጥርብናል የሚል እምነት ነበራቸው፡፡ አምር ኢብን ኣስ ሀገሪቱን በያዘ በጥቂት ወራት ውስጥም ግብጻዊያኑ ለወንዙ መስዋእቱን ለማቅረብ እንደሚፈልጉ ነገሩት፡፡ አምር ጉዳዩን ለብቻው ለመወሰን ባለመቻሉ ለኸሊፋው ዑመር ቢን ኸጣብ ደብዳቤ በመጻፍ አንድ ነገር እንዲያደርጉ ጠየቃቸው፡፡ ዑመርም “እንዲህ ዓይነት ኢሰብአዊ የሆነ ድርጊት መከወን በጭራሽ አይፈቀድም” በማለት ውሳኔያቸውን አሳወቁት፡፡ አምርም ለግብጻዊያኑ ይህንኑ ነገራቸው፡፡ በመሆኑም ለናይል ወንዝ ልጃገረድ የመሰዋቱ ድርጊት ተከለከለ፡፡
ታዲያ በዚያ ዓመት የናይል ወንዝ ፍሰት በጣም ቀነሰ፡፡ ግብጻዊያኑም በተፈጠረው ሁኔታ ተጨነቁ፡፡ ወደ አምር በመሄድም “ወንዙ ፍሰቱን የቀነሰው የዓመቱን መስዋእት ስላላገኘ ነው፤ ስለዚህ ልጅቷን እንድንሰዋለት ይፈቀድልን”  በማለት ወጠሩት፡፡ አምርም የተፈጠረውን ሁኔታ ለኸሊፋ ዑመር በደብዳቤ አሳወቃቸው፡፡ ይሁንና ኸሊፋው አቋማቸውን የሚቀይሩ አልሆኑም፡፡ ስለዚህ የሚከተለውን መልዕክት በደብዳቤ አስጻፉ፡፡
  “ይድረስ የአላህ ፍጥረት ለሆነው የናይል ወንዝ! በአላህ ፈቃድ የምትፈስ ከሆነ እንደ ድሮው እንድትፈስልን አላህን እንለምናለን፤ በራስህ ፈቃድ የምትፈስ ከሆነ ግን ውሃህን መያዝ ትችላለህ፤ እኛም አንፈልግህም፡፡”
ዑመር ደብዳቤውን ለአምር በመላክ በወንዙ ውስጥ እንዲጨምረው አዘዙት፡፡ አምርም ግብጻዊያኑን ሰብስቦ መልዕክቱን አነበበላቸውና ኸሊፋው ያዘዙትን ፈጸመ፡፡ ከትንሽ ወራት በኋላም ናይል በሙሉ አቅሙ መፍሰስ ጀመረ፡፡ ግብጻዊያኑም ወንዙ በራሱ ሃይል እንደማይፈስ በማረጋገጥ ከፈርዖኖች ዘመን ጀምሮ ሲፈጽሙት የነበረውን አጉል ድርጊት አስወገዱ፡፡
       *****
በዚያ ዘመን የግብጽ ዋና ከተማ እስክንድርያ ነበረች፡፡ እስክንድርያ በባህር ላይ የተቆረቆረች መሆኗ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ሮማዊያን በባህር በመምጣት ከተማዋን በድንገተኛ ጥቃት ሊያጠፏት እንደሚችሉ የተገነዘበው አምር ቢን ኣስ በውስጠኛው የሀገሪቱ ክፍል አዲስ መዲና ለመቆርቆር ወሰነ፡፡ ለዚህ የተመረጠው ደግሞ ከእስክንድርያ በ200 ኪ.ሜ. የሚርቅ ቦታ ነው፡፡ አምርም አዲሷን ከተማ በ641 መሰረተ፡፡ መስጊድ፣ ለቢሮ የሚያስፈልጉ ቤቶች፣ መኖሪያ ቤቶች፣ የወታደሮች ካምፕ ወዘተ በከተማዋ ውስጥ ተሰሩ፡፡ ለከተማዋም “ፉስጣጥ” የሚል ስም ተሰጠ፡፡
ፉስጣጥ በናይል ወንዝ ምስራቃዊ ዳርቻ ላይ በነበረችው በሮማዊያኑ የ“ባቢሎን” ከተማዋ ጎን ነው የተሰመረተችው፡፡ ይህች ከተማ ለሶስት መቶ ዓመታት የግብጽ ዋና ከተማ በመሆን አገልግላለች፡፡ በነዚያ ዓመታት በሙስሊሞች የኺላፋ ግዛት ግንባር ቀደም ከሆኑ የትምህርትና የንግድ ማዕከላት አንዷ ነበረች፡፡ የእስልምና ስነ-መለኮት ህግ (ፊቅህ) ሊቅና የሻፊዒያ መዝሐብ መስራች የነበሩት ታላቁ ምሁር ሙሐመድ ኢብን ኢድሪስ አሽ-ሻፊዒ በመጨረሻ የህይወት ዘመናቸው የኖሩትና የሞቱት በዚህች ከተማ ነው፡፡ ታዋቂው የታሪክ ምሁር ዓሊ ኢብን ሁሴይን አል-መስዑዲም አብዛኛውን ህይወቱን ያሳለፈውና ሞቶ የተቀበረው በፉስጣጥ ነው፡፡
       *****
በ910 ገደማ በምድረ-ግብጽ የተመሰረተው የፋጢሚይ ስርወ መንግሥት (Fatimid Dynasty) መሪዎች ፉስጣጥን አልወደዷትም፡፡ “ከተማዋ ቅርጽ ቢስ ስለሆነች ውብ ፕላን ያላት ዋና ከተማ ሊኖረን ይገባል” በማለት በ967 ከፉስጣጥ በስተሰሜን 30 ኪሎሜትር ያህል በሚርቅ ቦታ ላይ አዲስ ዋና ከተማ መሰረቱ፡፡ ለአዲሷ ከተማም “አል-ቃሂራ (Cairo) የሚል ስም ሰጡ፡፡ ፉስጣጥም ዝናዋንና እውቅናዋን በአዲሷ ከተማ ተቀማች፡፡
ያም ቢሆን ግን ፉስጣጥ የንግድ ማዕከል በመሆን መስራቷን ቀጥላለች፡፡ ለዚህም የረዷት በከተማዋ ተስፋፍተው የነበሩት የመስተዋት፣የልብስና የሸክላ ስራ ኢንዱስትሪዎች ናቸው፡፡ በ1168 የመስቀል ጦረኞች (Crusaders) ግብጽን ሲወሩ የከተማዋን ህልውና የሚፈታተን አደጋ ተደቀነ፡፡ ከተማዋ እንደሌሎች የመካከለኛ ዘመን ከተሞች የመከላከያ ግንብ አልነበራትም፡፡ ስለዚህ የግብጽ መሪዎች ከተማዋ በጦረኞቹ እጅ ከምትወድቅ ብትቃጠል ይሻላል በማለት ነዋሪቿን ወደ ካይሮ ካዘዋወሩ በኋላ የአምር ቢን ኣስ መስጊድ ካለበት ክፍል በስተቀር የተቀረውን የከተማዋን ክፍል አቃጠሉት፡፡
    ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን ፉስጣጥ በእዉቁ የጦር ጀግና በሰላሃዲን አዩቢ ትዕዛዝ መሰረት እንደገና አንሰራርታለች፡፡ ሆኖም ሰላሃዲን ከተማዋ ለብቻዋ እንድትጓዝ አልፈለገም፡፡ በክፉም ሆነ በደጉ ከዋና ከተማዋ ጋር መሄድ አለባት በማለት ከካይሮ ከተማ ጋር እንድትዋሃድ መሰረቱን ጣለ፡፡ በመሆኑም ጥንት ለብቻዋ የከተመችው ፉስጣጥ እያደር በአዲሷ የካይሮ ከተማ ተዋጠች፡፡
  “ፉስጣጥ” በአሁኑ ጊዜ “መስር አል-አጢቃ” የሚባለው የካይሮ ከተማ ጥንታዊ ክፍል አካል ናት፡፡ የጥንቱ የአምር ቢን ኣስ መስጊድ ወደ ካይሮ ሊገባ የቻለውም ከተማዋ በካይሮ በመጠቅለሏ ነው፡፡
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 4/2007



ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
በፎቶው ላይ የምትመለከቱት ለአፍሪቃ አህጉር የመጀመሪያ የሆነውን መስጊድ ነው፡፡ ይህ መስጊድ የተሰራው በ641 ሲሆን የሚገኘውም በግብፅ መዲና ካይሮ ውስጥ ነው፡፡ መስጊዱ የሚጠራው በመስራቹ በ“አምር ኢብን ኣስ” ስም ነው፡፡ ይሁንና አምር እና ጓዶቹ መስጊዱን የሰሩት በአል-ፉስጣጥ እንጂ በካይሮ አልነበረም፡፡ ታዲያ መስጊዱን ወደ ካይሮ ማን ነው ያስገባው?… እስቲ የዛሬ ወጋችንን በአምር ታሪክ እንጀምርና ስለፉስጣጥም ትንሽ እናውራ፡፡
       *****
አምር ኢብን ኣስ የዐረቢያ ምድር ካበቀለቻቸው ታላላቅ ፖለቲከኞችና የጦር መሪዎች አንዱ ነው፡፡ የተወለደው በመካ ከተማ ሲሆን ነቢዩ ሙሐመድን (ሰ.ዐ.ወ) ያፈራው የቁረይሽ ጎሳ አባል ነው፡፡ አምር የጉርስምና ዘመኑን እንደ ሌሎቹ የዐረቢያ ወጣቶች በግመል ግልቢያና በፈረስ ጉግስ አላሳለፈም፡፡ የርሱ ቀልብ ወደ ንግዱ ነበር ያተኮረችው፡፡ በመሆኑም  በዘመኑ በገበያ ውስጥ ተፈላጊ የሆኑ ሸቀጦችን ለማምጣት ወደ የመንና ሻም (ሶሪያ) በብዛት ይመላለስ ነበር፡፡ ሀብቱ እየተስፋፋ ሲሄድ ደግሞ እስከ ፋርስ (ፐርሺያ)፣ መስር (ግብፅ)፣ አቢሲኒያ (ሐበሻ/ኢትዮጵያ) እና ኦማን ድረስ እየሄደ ሸቀጦችን ያመጣ ጀመር፡፡ በነዚህ ሀገራትም በርካታ የንግድ ሸሪኮችን ለመፍጠር ቻለ፡፡ በሸሪኮቹ በኩልም ከየሀገራቱ ገዥዎች ጋር በመተዋወቅ ልዩ ልዩ ገጸ-በረከቶችን ይወስድላቸው ነበር፡፡
Mosque of Amr in Old Cairo in 19th Century
ይህ በእንዲህ እንዳለ ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) በ610 ገደማ እስልምናን ማስተማር ጀመሩ፡፡ የዐረብ ጎሳዎች የድንቁርና ህይወታቸውን ትተው እንደ ጥንቱ ቅድመ-አያቶቻቸው እንደ ነቢዩ ኢብራሂምና እንደ ዒስማዒል ፈጣሪን ብቻ እንዲገዙ ሰበኩ፡፡ ጥቂት ሰዎች እምነቱን ተቀበሉ፡፡ አብዛኞቹ ግን “የአባቶቻችንን መንገድ ልታስተወን ነው እንዴ…?” በማለት በነቢዩ ላይ በጠላትነት ተነሱባቸው፡፡ በነቢዩ ያመኑትንም ያሰቃዩ ጀመር፡፡ ነቢዩ በተከታዮቻቸው ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ሊከላከሉላቸው አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ከተከታዮቻቸው መካከል የተወሰኑትን በሚስጢር ጠርተው ወደ ሐበሻ (ኢትዮጵያ) እንዲሰደዱ አዘዟቸው፡፡ በዚሁ መሰረት አንድ መቶ የሚሆኑ ሰዎች ወደ ሐበሻ ተሰደዱ፡፡
የቁረይሽ ባላባቶች የነብዩ ተከታዮች ወደ ሐበሻ መሰደዳቸውን ሲሰሙ “እዚያ ሄደው ሳይደራጁ በቶሎ ልናስመልሳቸው ይገባል” በማለት አንድ የልዑካን ቡድን ወደ አክሱም ሰደዱ፡፡ ቡድኑ ሁለት አባላት የነበሩት ሲሆን እነርሱም አምር ቢን ኣስ እና አብዱላህ ቢን ረቢዓ ናቸው፡፡ ያ ቡድን በሚችለው መንገድ ሁሉ ተደራድሮ የሐበሻውን ንጉሥ አርማህን (አስሓማ) በማሳመን የነቢዩን ተከታዮች ወደ መካ እንዲያስመልስ ታዟል፡፡ ነገር ግን ወደ ሐበሻው ንጉሥ ቀርቦ ድርድሩን እንዲፈጽም ስልጣን የተሰጠው ለአምር ቢን ኣስ ነው (አብዱላህ ቢን ረቢዓ “አምር” መልዕክቱን በትክክል ማድረሱን እንዲታዘብ ብቻ የተላከ ነው የሚመስለው)፡፡

አምር በንግድ ሰበብ ወደ ኢትዮጵያ በተመላለሰባቸው ዓመታት ከሐበሻው ንጉሥ ጋር ለመተዋወቅ ችሏል፡፡ ሆኖም አምር ለድርድሩ የተመረጠው በዚህ ብቻ ሳይሆን በዘመኑ ከነበሩት የመካ መኳንንት መካከል ተናግሮ በማሳመን ብቃቱ የተዋጣለት ሆኖ በመገኘቱም ጭምር ነው፡፡
       *****
አምር ከንጉሡ ዘንድ ቀርቦ ባደረገው ድርድር ያሰበው አልተሳካለትም፡፡ ንጉሡ ስደተኞቹን ለማንም አሳልፎ እንደማይሰጥ እቅጩን ነግሮታል፡፡ ይሁንና አምር በዚህ ተበሳጭቶ ወደ አክሱም መምጣቱን አላቆመም፡፡ ከድርድሩ በኋላም ቢሆን ለሁለት ጊዜያት ወደ ሐበሻ መጥቷል፡፡ ታዲያ ለመጨረሻ ጊዜ ከንጉሡ ጋር በተገናኘበት ጊዜ ንጉሡ እንዲህ ሲል መከረው፡፡
  “አምር ሆይ! አንተን የመሰለ ሰው የነቢዩ ሙሐመድን ትምህርት አልቀበልም ሲል ይገርመኛል፡፡ እናንተ ዐረቦች ከማንኛውም ህዝብ ወደ ኋላ ቀርታችኋል፤ ሙሐመድ ያመጣው ዐረቢያን ከጭለማ የሚያወጣውን አዲስ ብስራት ነው፡፡ በእርሱ ያመነ ሰው በፈጣሪ ዘንድ ከሚያገኘው ምንዳ በተጨማሪ ይህችን ዓለም ይገዛል፡፡”
ንጉሥ አርማህ አምርን እንዲህ ብሎ በሚመክርበት ጊዜ ለራሱም የነቢዩን እምነት ተቀብሏል፡፡ ይሁንና መላው የሐበሻ ህዝብ አዲሱን እምነት እንዲቀበል አዋጅ አልነገረም (አንዳንድ ጸሐፊያን “ንጉሥ አርማህ በነቢዩ ማመኑን በሚስጢር ይዞት ነበር” ይላሉ)፡፡
       *****
አምር ከሐበሻው ንጉሥ ከተለየ በኋላ በቀጥታ ወደ መካ ነው ያመራው፡፡ እዚያም ታዋቂው ጀግና ኻሊድ ቢን ወሊድ (ረ.ዐ) ወደ መዲና ለመሰደድ ሲዘጋጅ አገኘውና ከርሱ ጋር መሄድ እንደሚፈልግ ነገረው፡፡ ኻሊድም ሀሳቡን በደስታ ተቀበለው፡፡ ሁለቱ ሰዎች መዲና በደረሱ ጊዜ ነብዩ ሁለቱንም ሸሃዳ አስያዟቸው፡፡ ይሁንና ነቢዩ እነዚህን የዐረቢያ ጎምቱዎች አላሳረፏቸውም፡፡ ኻሊድን በሰሜን በኩል በነቢዩ መንግሥት ላይ አደጋ የጋረጡትን ሮማዊያንን ለመዋጋት በሚዘምተው የዘይድ ቢን ሓሪሳ ቡድን ውስጥ ቀላቀሉት፡፡ አምር ቢን ኣስ ደግሞ ወደ ኡማንና ባህሬን ሄዶ የዲፕሎማሲ ስራ እንዲሰራ አደረጉት፡፡ አምር ወደ ኡማን (ኦማን) የተጓዘው እነ አቡበከር፣ ዑመር እና አቡ ኡበይዳን (ረ.ዐ) የመሳሰሉ ታላላቅ ሰዎች የተካተቱበትን ቡድን በመምራት ነው፡፡ ነቢዩ አምር የቡድኑ መሪ እንዲሆን ያደረጉት የዲፕሎማሲ ችሎታውን በሚገባ ያውቁት ስለነበረ ነው፡፡ አምርም የዲፕሎማሲ ስራውን በደንብ ከመፈጸሙም በላይ የኦማን ሰዎች ወደ እስልምና እንዲገቡ ለማድረግ ችሏል፡፡
       *****
አምር ከነቢዩ ህልፈት በኋላም በአቡበከርና በዑመር ኺላፋዊ መንግሥት ውስጥም አገልግሏል፡፡ በጦር ግንባርም ሆነ በዲፕሎማሲ ስራ አንቱታን ያጎናጸፉትን ተግባራት ፈጽሟል፡፡ ከአምር ጋር የሁልጊዜ ተጠቃሽ ሆኖ የዘለቀው ግን ሮማዊያንን ከግብጽ በማባረር ወደ ኸሊፋዎቹ ግዛት የቀላቀለበት ዘመቻው ነው፡፡
አምር የግብጽን ዘመቻ (the conquest of Egypt) ያመነጨው በራሱ ነው ይባላል፡፡ በመሆኑም ኸሊፋ ዑመር ቢን ኸጣብ ሐሳቡን ተቃውመውት ነበር፡፡ የዑመር ተቃውሞ ዘመቻውን በመጥላት ሳይሆን “በተለያዩ ግንባሮች የተበተኑትን ወታደሮቻችንን በቶሎ አሰባስበን በዘመቻው እንዲሳተፉ ለማድረግ አንችልም” ከሚል የመነጨ ነው፡፡ ይሁንና አምር በወቅቱ በነበሩት ወታደሮች ብቻ ዘመቻውን በመጀመር ተጨማሪ ጦርን መጠባበቁን ነው የመረጠው፡፡
 
  አምር በ639 ዓ.ል በአራት ሺህ ወታደሮች የሲናይ በረሃን አቋረጠ፡፡ ሮማዊያንን በድንገተኛ ጥቃት በማራወጥ “ቢልቢስ” እና “ባቢሎን” በሚባሉት ስፍራዎች አሸነፋቸው (ይህቺ የግብጿ “ባቢሎን” የኢራቋ “ባቢሎን” አምሳያ እንድትሆን በሮማዊያን የተፈጠረች ናት)፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላ ደግሞ በጥንቷ የኦኑ ከተማ (በፈረንጆች አጠራር Heliopolis) አጠገብ አሸነፋቸው፡፡ ከአንድ አመት በኋላ 12,000 ወታደሮች ከሶሪያ ሲመጡለትም አምር የዘመኑ የአፍሪቃ ታላቅ ከተማ የነበረችውን እስክንድርያን (አሌክሳንደሪያ) ለመያዝ ዘመተ፡፡ ሮማዊያን በከተማዋ ከሰማኒያ ሺህ የሚበልጥ ጦር የነበራቸው ቢሆንም ከነርሱ በአምስት እጥፍ በሚያንሰው የአምር ቢን ኣስ ጦር ድል ተመቱ፡፡ ግብጽም ሙሉ በሙሉ የሙስሊሞቹ ኺላፋ አካል ሆነች፡፡
ታዲያ አምር ግብፅን በአንድ ዓመት ውስጥ ለመያዝ የበቃው በጦር ሃይሉ ጥንካሬ ብቻ አልነበረም፡፡ በወቅቱ የግብጽ ክርስቲያኖች ከፍተኛ እርዳታ ስላደረጉለት ጭምር ነው ታላቁን ድል ለማጣጣም የበቃው፡፡ ክርስትያኖቹ አምርን የደገፉበት ምክንያት አለ፡፡
  ግብጻዊያን ክርስቲያኖች የሚያምኑበት የ“ተዋሕዶ” እምነት “ክርስቶስ የሁለት ባህሪ ባለቤት ነው” ከሚለው የሮማዊያን ክርስትና ይለያል፡፡ በዚህም ምክንያት ሮማዊያኑ የግብጽ ክርስቲያኖችን እንደ “መናፍቃን” ያዩዋቸው ነበር፡፡ ከቁስጥንጥንያ (የአሁኗ ኢስታንቡል) ተሹመው ግብጽን የሚገዙት እንደራሴዎችም የግብጽ ክርስትያኖች እምነታቸውን እንዲለውጡ ለማድረግ በልዩ ልዩ መንገዶች ይጨቁኗቸው ነበር፡፡ አንዳንዴም ፓትሪያኮቻቸውን እያሰሩ “እምነትህን ተው” እስከማለት ይደርሳሉ፡፡ አምር ቢን ኣስ ግብጽን ለመያዝ በሚዘምትበት ዘመን እንኳ የግብጽ ፓትሪያርክ የነበሩት “አቡነ ብንያም” (ቤንጃሚን) ከሀገር ተባረው ነበር፡፡ በመሆኑም ግብጻዊያኑ ከጭቆናው ለመገላገል ሲሉ አምር ቢን ኣስን በዘመቻው በእጅጉ ረድተዋል፡፡ (በነገራችን ላይ ከ5ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ ግብጽን ይገዟት የነበሩት ሮማዊያን መቀመጫውን በሮም ከተማ ያደረገው የታላቁ ኢምፓየር አካል አልነበሩም፡፡ የሮም ኢምፓየር በ395 “ምስራቅ” እና “ምዕራብ” ተብሎ ለሁለት ተከፍሏል፡፡ የሮማ ከተማ በ476 በጀርመን ጎሳዎች ስትወረር የምዕራቡ ኢምፓየር ህልውና አክትሟል፡፡ የምስራቁ ኢምፓየር ግን እስከ 1431 ድረስ ቆይቷል፡፡ ብዙዎች የምስራቁን ኢምፓየር የሚጠሩት “ቤዛንታይን” በሚል ስም ነው፡፡ ሆኖም ዐረቦችም ሆኑ የኢምፓየሩ ነዋሪዎች ግዛቱን “ሮም” እያሉ ስለሚጠሩት እኔም ይህንን ልማድ ተከትያለሁ)፡፡  

  አምር ግብጽን በሚያስተዳድርበት ጊዜ በክርስትያኖቹ ላይ ይደርስ የነበረውን ጭቆና ሙሉ በሙሉ አስወግዷል፡፡ በህዝቡ ላይ በየምክንያቱ ይጣሉ የነበሩትን ልዩ ልዩ የታክስ ዓይነቶች በማስቀረት ሁሉም ዜጎች ዓመታዊውን “ዑሽር” (አስራት) እና “ዘካት” ብቻ እንዲከፍሉ አድርጓል፡፡ በመንግሥቱ ቢሮክራሲ ውስጥም ክርስትያኖቹን አሳትፏል፡፡ የቤተ-ክርስቲያኖች ይዞታ የሆኑ መሬቶችና ንብረቶች እንዲከበሩም አድርጓል፡፡
       *****
 አምር ቢን ኣስ ግብጽን ማስተዳደር በጀመረ በዓመቱ ነው “አል-ፉስጣጥ” የተባለችውን ከተማ የቆረቆረው፡፡ ስለ“አል-ፉስጣጥ” ምስረታና ስለሌሎች ጉዳዮች በሚቀጥለው ክፍል እናወጋለን፡፡
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 3/2007
ገለምሶ-ሀረርጌ



አፈንዲ ሙተቂ
      —–
      የህንድ ፊልም ማየት የጀመርኩት በ1978 ይመስለኛል፡፡ በዘመኑ ቶማስ የሚባል የህንድ ክልስ ነበር፡፡ ይህ ሰው ፊልሞቹን ከድሬ ዳዋ ያስመጣና በሌሎች የሀረርጌ ከተሞች እያዞረ በፕሮጀክተር ያሳያል፡፡ በዘመኑ “የአሜሪካ ፊልም ውሸት ነው፤ የህንድ ፊልም እውነት ነው” የሚል አስተሳሰብ ስለነበረ የሰዎች ምርጫ በአብዛኛው የህንድ ፊልም ነበር፡፡ በመሆኑም ቶማስ ከሚያሳያቸው ፈልሞች መካከል ከመቶ ዘጠና የሚሆኑት የህንድ ፊልሞች ነበሩ፡፡ 
   በዚህም መሰረት ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት የህንድ ፊልም “T.D” የሚል ርዕስ የነበረው ሲሆን አክተሩም “ጄተንድራ” ነው (በኋላ ላይ እንደተረዳሁት ያ ፊልም First Blood  ከሚባለው የራምቦ ፊልም የተቀዳ ነው)፡፡ ቶማስ ፊልሙን የሚያሳየው በሁለት ብርና በሶስት ብር ነው፡፡ በቶማስ ሲኒማ ስር ካየኋቸው ሌሎች የህንድ ፊልሞች መካከል Disco Dancer, Jimmy and His Elephant, Mard የተሰኙት ይታወሱኛል፡፡  
        በ1981 የአውራጃችን አኢወማ ቪዲዮ ሲያስመጣ ግን የቶማስ ሲኒማ “በጣም ውድ ነው” በሚል ተረሳ፡፡ ቶማስም ወደኛ መምጣቱን ተወ፡፡ በዚህም መሰረት Mister India, Ashanti, Kassam Paeda, Love Story, የመሳሰሉ ፊልሞችን በአኢወማ አየን፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ “ፎቶ ማወርዲ” የሚባለው ፎቶ ቤት ሌላ ቪዲዮ ማሳያ ከፈተና ከአኢወማ ጋር ፉክክር ውስጥ ገቡ፡፡ ሁለቱም በርካታ ፊልሞችን አስኮመኮሙን፡፡ በፎቶ ማወርዲ ካየኋቸው ፊልሞች መካከል “Ter Kassam”, “Maa Kassam”, “Numberi Admi”, “Khoj”, “Marry Kassam”, “My Name is Lakan”, “Tarzan”, “Coolie”, የሚባሉትን ከነ ስሞቻቸው አስታውሳቸዋለሁ፡፡ የብዙዎቹን ስም ግን አላስታውስም፡፡
*****  *****  *****
        በህንድ ፊልሞች የምናውቃቸው አክተሮች በከተማችን በትክክለኛ ስማቸው አልነበረም የሚጠሩት፡፡ አንዳንዶቹ እኛ ባወጣንላቸው ስሞች ነው ይበልጥ የሚታወቁት፡፡ ለምሳሌ “ሚቱን ቻካርቦርቲ” የሚባለው አክተር “ጂሚ” በሚለው ስም ነው የሚታወቀው፡፡ “ዳርሜንድራም” በኛ አጠራር “ሻንካር” ነው የሚባለው፡፡ “ሪሽ ካፑር” ደግሞ “ኮጅ” እየተባለ ነው የሚጠራው፡፡ እውነተኛ ስሙ “ሰኒ” የሆነው አክተር ደግሞ በኛ አጠራር “ገባር” ነው የሚባለው፡፡ “አጄይ ኩማር”ም “ላቭ ስቶሪ” ተብሎ ነበር የሚጠራው፡፡ ከነዚህ ስሞች መካከል አንዳንዶቹ (እንደ “ጂሚ” እና “ሻንካር” ያሉት) አክተሩ ታዋቂ በሆነበት ፊልም ውስጥ ከሚጠራበት ስም ነው የተወሰዱት፡፡ እንደ “ኮጅ” እና “ላቭ ስቶሪ” የመሳሰሉት ደግሞ አክተሮቹ የተወኑባቸው ፊልሞች አርዕስት ናቸው፡፡    
        ከዚህ ሌላ አክተሩ በፊልሙ ውስጥ ሲያንጸባርቀው የነበረውን ድርጊት በመመልከት የተሰጡ ስሞችም አሉ፡፡ ለምሳሌ “አኒል ካፑር” የሚባለው አክተር በአንድ ፊልም ውስጥ ያለ ማቋረጥ “ማስቲካ” ያኝክ ስለነበረ “ማስቲካ” ተብሎ ተሰይሟል፡፡ “ቆሮንዴ” ደግሞ “Sholay” በተሰኘው የአሚታብ ባችቻን ፊልም ውስጥ በአፍ የሚታኘክ ትምባሆ ስለሚጠቀም ነው እንዲህ ተብሎ የተጠራው (“ቆሮንዴ” በአፍ የሚታኘክ የትምባሆ ዐይነት ነው)፡፡ እንደ ከማል ሐሰን፣ ነስሩዲን፣ አሚታብ ባችቻን፣ ሻሽ ካፑር፣ ጄክ ሸሪፍ፣ ጎቪንዳ፣ ሳንጃይ የመሳሰሉትን ግን በትክክለኛ ስማቸው ነው የምንጠራቸው፡፡
     ታዲያ በጣም ያስገረመኝ ይህ በኛ ከተማ የምንጠቀምበት የስም አጠራር ዘይቤ ድሬ ዳዋና ሀረርን ጨምሮ በሌሎች ከተሞችም በስፋት የሚታወቅ መሆኑ ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ ያደረግኩት ጥናት እንደሚያመለክተው ከስሞቹ መካከል አንዳንዶቹን እኛ መፍጠራችን ትክክል ቢሆንም ሌሎቹ ስሞች ከድሬ ዳዋ ልጆች የተኮረጁ ናቸው፡፡
      በድሮው ዘመን “አክተር” የምንለው በፊልሙ ውስጥ መልካም ስብዕና የሚያሳየውን ብቻ ነው፡፡ እኩይ ባህሪ ተላብሶ የሚተውነው በኛ ቋንቋ “ሙጅሪም” ነው የሚባለው፡፡ በአንደኛ ደረጃ ከሚነሱ ሙጅሪሞች መካከል “አሻንቲ”፣ “ሻክቲ”፣ “ጃሉ”፣ “ሼራ”፣ “ቆሮንዴ”፣ “ፋሩቅ” የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ (ፋሩቅ Disco Dancer በተሰኘው ዝነኛ የጂሚ ፊልም ውስጥ የተወነው ወፍራም ሙጅሪም ነው፤ አስታወሳችሁት አይደል?)፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ከሚመደቡ ሙጅሪሞች መካከል ደግሞ “ሳምሶን መላጣ” እና “መለኪያ” የተባሉት ይጠቀሳሉ:: እነዚህኛዎቹ ሙጅሪሞች በአብዛኛው በታላላቆቹ ሙጅሪሞች እየታዘዙ ጥፋት የሚፈጽሙ ናቸው፡፡ ከማል ሐሰንም ሲያሻው ከነዚህ ጋር ይደመርና ሙጅሪም ይሆናል፡፡
      በህንድ ፊልም ውስጥ ዘወትር የሚታይ ሶስተኛ አክተር አለ፡፡ ይህ ሰው በፊልሙ ውስጥ የሚሰጠው ሚና እንደ ቤተሰብ አጫዋች ሆኖ ሰዎችን ማሳቅ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አስቂኝ ገጸ-ባህሪ በያኔው አጠራር “ማህሙዴ” ይባላል፡፡ እጅግ ዝነኛ ከሆኑ ማህሙዴዎች መካከል “ሻክቲ” ተጠቃሽ ነው (“ሻክቲ” ሲፈልግ “ሙጅሪም”፤ ሲያሻው ደግሞ ማሕሙዴ ይሆናል)፡፡
*****  *****  *****
        የህንድ ፊልም ልዩ ገጽታው በርካታ ዘውጎችን አንድ ላይ የሚደበላልቅ መሆኑ ነው፡፡ የአክሽን ፊልም ውስጥ ኮሜዲ አለ፣ አስማት አለ፣ ሮማንስ አለ፤ ዳንስ አለ፤ በአንዱ ፊልም ውስጥ ሁሉም ነገር ይገኛል፡፡ ደግሞም አክተሮቹ ሲደንሱ ድምጻቸው አንድ ዓይነት መሆኑ በጣም ያደናግራል፡፡ የሴትም ሆነ የወንድ ድምጽ ለመለየት ያስቸግራል፡፡
      ከዚህ በተጨማሪ የህንድ ፊልም ውስጥ የሚታየው ግነት ከፍተኛ ነው፡፡ ለምሳሌ Mard በተሰኘው ፊልም ውስጥ አሚታብ ለመብረር የሚያኮበኩበውን ሂሊኮፕተር በገመድ ጠልፎ እንዳይበር ያደረገበት ትዕይንት ዘወትር አይረሳኝም፡፡ በልጅነታችን ያንን ትዕይንት እንደ ጉድ ነበር ያጨበጨብንለት፤ አሁን ቢሆን ግን “አንተ ውሸታም! ሞኝህን ፈልግ ” ብዬ ቪዲዮውን የምዘጋው ይመስለኛል፡፡
      የህንድ ፊልም ሲነሳ ዘወትር የሚታወሱኝ ሁለት ልጆች አሉ፡፡ አንደኛው ታገል ዲሪብሳ ይባላል፡፡ ሌላኛውን ልጅ ግን ስላላስፈቀድኩት ስሙን አልነግራችሁም፡፡ ታገል ምን አደረገ መሰላችሁ?.
     የጄተንድራን ፊልም እያየን ነበር፡፡ በፊልሙ መሀል ላይ ሻክቲ የተባለው ሙጅሪም የጄተንድራን እህት በመኪና ካሯሯጣት በኋላ ይገድላታል፡፡ ትዕይንቱ በጣም ያሳዝናል፡፡ በተለይ ልጅቷ በደም አበላ ተነክራ ላያት ሰው ልብ ትሰብራለች፡፡ ይሁን እንጂ ብዙዎቻችን ፊልም መሆኑን አልሳትንም፡፡ ታገል ግን ከመመሰጡ ብዛት የእውነት ትዕይንት መሰለው፡፡ እናም ጮክ ብሎ “ህግ የለም እንዴ?” አለ፡፡ በቪዲዮ ቤቱ የነበረው ሰው ሁሉ በሳቅ ፍርስ አለ፡፡
      የሁለተኛው ሰው ማስታወሻዬ ግን ከዚህ ይብሳል፡፡ በጊዜው ከነበሩት የሀብታም ልጆች ነን ባዮች መካከል አንዳንዶቹ የለየላቸው ጅላጅሎች ነበሩ፡፡ አሪፍ መኪና ሲያዩ “የዘመዳችን ናት” ማለት ይቀናቸዋል፡፡ “ነዋይ ደበበ ቤታችን ሊመጣ ነው” የሚሉም ነበሩ፡፡ እኛም ለነዚህ ጅሎች ነገር እያሟሟቅን ብራቸውን እናጫርሳቸው ነበር፡፡ ከነዚያ ልጆች አንዱ “አሚታብ ዘመዳችን ነው” እያለ ያወራልን ነበር፡፡ እኛም እያወቅን እንሞኝለታን:: አብዛኛውን ጊዜ የፊልም መግቢያ ዋጋውን የሚከፍልልን እርሱ ስለሆነ ለርሱ መሞኘታችን የግድ ነበር፡፡
      ታዲያ በብዙ ፊልሞች ውስጥ ሲሞት የማይታየው “ጀግናው” አሚታብ ባችቻን ሲያቀብጠው Sholay በተሰኘው ፊልም መጨረሻ ላይ ሞተ፡፡ ነገሩ በጭራሽ ያልተገመተ በመሆኑ ብዙዎች ተገረሙ፡፡ “ጉድ ነው! አሚታብም ይሞታል እንዴ?”… ተባባልን፡፡ እኛ እንዲህ ያልነው “አሚታብ ወክሎት የሚጫወተው ገጸ-ባህሪ ዘወትር አይሞትም” ከሚል መነሻ ነበር፡፡ ያ የኛ ስፖንሰር የሆነው ልጅ ግን እየየውን አቀለጠው፡፡ “ዘመዴ ሞቶ የት አባቴ ነው የምገባው?” እያለ አነባ፡፡ ፊልም ለመመልከት የሄደው ሰው ግራ ተጋባ፡፡ ለምን እንደሚያለቅስ ብንነግራቸው ሁላችንንም እንደ ጅል ይቆጥሩናል ብለን ፈራን፡፡ ስለዚህ ቶሎ ብለን ልጁን ደጋግፈን ወደ ውጪ ካወጣነው በኋላ እያባበልነው ከቤታቸው ወሰድነው፡፡
   ይህ ትዕይንት በአሁኑ ዘመን ይከሰታል ተብሎ የማይታሰብ ነው መቼስ! ከዛሬ ሀያ አመት በፊት ግን ተመሳሳይ ድርጊቶችን ማየት የተለመደ ነው፡፡
—–
      የህንድ ፊልም ለመጨረሻ ጊዜ ያየሁት በ1995 ይመስለኛል፡፡ በወቅቱ ያየሁት Kabi Ghushi Kabi Gham የሚል የሻህሩኽ ኻን እና አሚታብ ፊልምን ነው፡፡ ያየሁበት ስፍራ አዲስ አበባ በመሆኑ ግን እኛ ስናደርግ እንደነበረው “ማህሙዴ፣ ሙጅሪም፣ ወዘተ…” እያለ ስለ ፊልሙ የሚተርክ ሰው አላጋጠመኝም፡፡ ከዚያ ወዲህ እኔና የህንድ ፊልም አንተዋወቅም፡፡ ለመሆኑ አሁን ምን ደረጃ ላይ ደርሷል?… እስቲ ስለ ህንድ ፊልም ያላችሁን ትዝታችሁ አካፍሉን፡፡
ሰላም!
የካቲት 17/2006
ሸገር


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
  ዛሬ በወግ ሽርሽር ብዙ ሀገር አቋርጠን “ፋርስ” ገብተናል፡፡ የዑመር ኻያም ሀገር! የፊርደውሲ ሀገር! የኒዛሚ ሀገር! የጃሚ ሀገር! የሓፊዝ ሀገር! በሩባኢያትና በገዛላት ዓለምን እያስፈነደቁ ለብዙ ክፍለ ዘመናት የዘለቁ የቅኔ ጠቢባን የተገኙባት ምድር!
  
   ዛሬ ፐርሺያ ነን! ዛሬ ኢራን ነን፡፡ ዛሬ ቴህራን ነን፡፡ ዛሬ ኒሻፑር ነን፡፡ ዛሬ ጠብሪዝ ነን፡፡ ዛሬ ሂልማንድ ነን፡፡ ዛሬ ኢስፋሓን ነን፡፡ ዛሬ ሺራዝ ነን! እዚያ ትልቅ የጥበብ ድግስ ተደግሶ ይጠብቀናል፡፡ እዚያ ከመድረሳችን በፊት ግን ለውዲቷ ኢራን ይህንን “ሩበእ” ብንቀኝላትስ?!  
አንቺ ሀገረ-ፋርስ የሀገር ጥበበኛ
ሁሉንም ያበቀልሽ አድርገሽ መልከኛ
የቅኔሽ መዓዛ ጠርቶኝ መጥቻለሁ
እጅሽን ዘርግተሸ መርሓባ በይኛ!
ሞክሬዋለሁ አይደል?. አዎን! “ሩበእ” (ሩባኢያት) ማለት እንዲህ ነው፡፡ ባለ አራት መስመር ቅኔ ሆኖ ሶስተኛው ስንኝ ከሌሎቹ አፈንግጦ ሲጻፍ በፋርሲ ቋንቋ “ሩበእ” ይባላል (ከዐረብኛው “ራቢዕ” የተገኘ ቃል ነው)፡፡ አንደኛ፣ ሁለተኛ እና አራተኛ መስመሮች በተመሳሳይ ፊደል ነው የሚያበቁት፡፡ ሶስተኛው ስንኝ ግን ከነርሱ ጋር አይገጣጠምም፡፡ “ሩበእ” ነጠላ ስም ነው፡፡ ለብዙ ቁጥር “ሩባኢያት” ይሆናል፡፡ አንዳንዶች የግጥሙ ዘውግ ከዐረቢያ ነው የተወረሰው ቢሉም “ሩባኢያት” ኦሪጂናሌ የኢራን የግጥም ዘይቤ መሆኑ በምሁራን ተረጋግጧል፡፡
ኢራናዊያን በሩባኢያት በጣም ይኮሩበታል፡፡ እንደ ብሄራዊ ቅርሳቸው ያዩታል፡፡ በተለይ The Zenith of Persian Literature በሚባለው ዘመን (ከ950 እስከ 1400 ድረስ) የተጻፉ ሩባኢያቶችን ከልብ ያፈቅሩአቸዋል፡፡ እኛም እንደ ዕድል ሆኖ በተስፋዬ ገሠሠ በኩል የዑመር ኻያም ሩባኢያትን በአማርኛ ለማንበብ በቅተናል፡፡ ዳሩ ግን እኛ ካጣጣምናቸው ሩባኢያት በላይ በኢራናዊያን የሚወደዱት የነ ሩሚ፣ ሳዲ፣ ጃሚ እና ሓፊዝ “ሩባኢያ”ት ናቸው፡፡ (ኢራናዊያን ከዑመር ኻያም በጣም የሚያደንቁለት የሒሳብ ሊቅነቱን ነው እንጂ ገጣሚነቱን አይደለም)፡፡
*****
ኢራን ነፍስ የሆነች ሀገር ናት! በጣም ውብ ባህልና የዳበረ ቋንቋ አላት፡፡ ታሪኳም ከቅድመ ክርስቶስ በፊት ከነበረው ዘመን ጀምሮ ነው የሚሰላው፡፡ በዚህ ረገድ ከመካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት በእድሜ እርሷን የሚቀድሙት የርሷ ጎረቤት ሀገራት የሆኑት ሜሶጶጣሚያ (ኢራቅ) እና ሶሪያ ብቻ ናቸው፡፡ ዓለምን ያስደመሙ ታላላቅ ባለቅኔዎችን በማብቀል ግን ኢራን ከሁሉም ሀገራት ትበልጣለች፡፡
ኢራን ከጥንትም ጀምሮ ትክክለኛ ስሟ “ኢራን” ነው፡፡ የርሷ ተወላጆች ሀገራቸውን በዚሁ ስም ነው የሚጠሯት፡፡ ነገር ግን አብዛኛው የዓለም ህዝብ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ “ፋርስ” ወይንም “ፐርሺያ” ይላት ነበር፡፡ ኢራናዊያኑ “ይህ ስም አንዱን ክፍለ ሀገር እንጂ ሀገሪቱን በሙሉ ስለማይወክል ሀገራችንን ፐርሺያ እንዳትሏት” የሚል ዘመቻ ከፍተው ተሳክቶላቸዋል፡፡ ዛሬ ይኸው ኢራን ትባላለች፡፡ ይሁንና ቋንቋው “ፋርሲ” ነው የሚባለው፡፡ በዚህ ላይ ኢራዊያኑ ተቃውሞ የላቸውም፡፡ እንግዲህ በዚህ የፋርሲ ቋንቋ ነበር እነዚያ ውድ ባለቅኔዎች ዓለምን በጥበብ ሲያጠምቁ የነበሩት፡፡
*****
   የጥንቷ ኢራን እንዲህ እንደ አሁኑ አልነበረችም፡፡ ዛሬ አፍጋኒስታን፣ ቱርክሜኒስታን እና አዘርባይጃን የሚባሉ ሀገራት ለብዙ ክፍለ ዘመናት የርሷ ግዛቶች ነበሩ፡፡ የዛሬው እንግዳችንም በአሁኗ አፍጋኒስታን፣ በበልኽ አውራጃ፣ “ሩማ” በምትባል ከተማ ነው የተወለደው፡፡ እውነተኛ ስሙ ጀላሉዲን ሙሐመድ ወለድ ነው፡፡ ብዙዎች እርሱን የሚጠሩት ግን በትውልድ ከተማው ስም “ሩሚ” በማለት ነው፡፡
የሩሚ አባት የታወቁ ሼኽ እና ቃዲ ነበሩ፡፡ ሩሚም መደበኛ ትምህርቱን እዚያው በአባቱ ስር መማር ጀመረ፡፡ ነገር ግን በአስራ አንድ ዓመቱ መጥፎ እጣ ገጠመው፡፡ በዘመኑ መካከለኛው እስያን ደም በደም አድርገው የነበሩት የሞንጎል ወራሪዎች ወደ “በልኽ” እየተቃረቡ መሆናቸው ተሰማ፡፡ ስለዚህ የሩሚ አባት ቤተሰቡን ይዞ በምዕራብ አቅጣጫ ተሰደደ፡፡ “ኒሻፑር” ከምትባለው ጥንታዊት የኢራን ከተማ ሲደርሱም ከዘመኑ ዝነኛ ገጣሚ ፈሪዱዲን አጣር ጋር ተገናኙ፡፡ አጣር በሩሚ ነገሮችን የማስተዋል ችሎታ ተደንቆ “ይህ ልጅ ለወደፊቱ ትልቅ ባለቅኔ የመሆን ተስፋ አለው” የሚል ትንቢት ተናገረ ይባላል፡፡
ከሞንጎል የሸሸው የሼኽ ሙሐመድ ባሀኡዲን ወለድ (የሩሚ አባት) ቤተሰብ በመጨረሻ “ኮኒያ” ከምትባለው የቱርክ ከተማ ደረሰ፡፡ ሼኽ ባሃኡዲን እዚያ ካለው መድረሳ ማስተማር ጀመሩ፡፡ እርሳቸው ከሞቱ በኋላ ደግሞ የማስተማሩ ተግባር አንጋፋ ልጃቸው ለሆነው ለሩሚ ተላለፈ፡፡ ይሁንና ልጁ በማስተማሩ ላይ ሊያተኩር አልቻለም፡፡ ተፈጥሮንና ኑሮን እያየ ይህንን ግልብጥብጥ ዓለም የፈጠረውን ፈጣሪ አፈቀረ፡፡ ለርሱ የሙገሳ ቃላትን በግጥም መደርደር ጀመረ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን አንድ ያልተጠበቀ እንግዳ ወደ ሩሚ መንደር ብቅ አለ፡፡
ሙላህ ሸምሱዲን ይባላል፡፡ የጠብሪዝ ተወላጅ ነው፡፡ ኢራናዊያን “ሸምስ-ኢ-ጠብሪዚ” ይሉታል፡፡ ሩሚ በሸምሱ-ጠበሪዝ ላይ ባየው መንፈሳዊ ልቅና ተመሰጠ፡፡ እንደ መምህሩም ቆጠረው፡፡ ቤተሰቡንና ስራውን ሁሉ ትቶ ከርሱ ጥበብን መቅሰም ጀመረ፡፡ አንድ ቀን ግን ሸምስ ጠብሪዝ እዚህ ነኝ ሳይል ጠፋ፡፡ በዚህም የተነሳ ሩሚ የመምህሩን ፍቅር ተራበ፡፡ ፍቅሩ እያቃጠለው “መደድ” (የፍቅር የመጨረሻ ደረጃ) ውስጥ አስገባው፡፡  ከዚያማ ማን ይቻለው! ከመምህሩ የተማረውን በራሱ ቋንቋ ጻፈው፡፡ 30,000 “ገዛል” እና ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ “ሩባኢያት”ን ከተበ፡፡ እነዚህም ግጥሞች “ዲዋን-ኢ-ሸምሹ-ጠብሪዝ” በተሰኘ መጽሐፍ በአንድ ላይ ተሰበሰቡ (“ገዛል” የሚባለው ግጥም “ዜማ” ጭምር እንዳለው ልብ በሉ)፡፡
*****
የሩሚ የጥበብ ፍቅር አላበቃም፡፡ በሸምስ ጠበሪዝ መጥፋት የተከፋችው ነፍስ ሌላ መምህር ፍለጋ አላቆመችም፡፡ ታዲያ ሩሚ ብዙም አልተጓዘም እዚያው “ኮኒያ” ከተማ ውስጥ ተማሪው የነበረ ልጅ መምህሩ ሆኖ ተገኘ፡፡
 ሑሳሙዲን ይባላል፡፡፡ ሑሳሙዲን ከሩሚ ግጥሞች ሌላ የነ ፈሪዱዲን አጣርን፣ የነ ሰነኢንና የሌሎች ታላላቅ የፋርስ ባለቅኔዎችን ስራ አጥንቷል፡፡ እናም አንድ ቀን ሩሚን እንዲህ አለው፡፡ “መምህር! የርስዎ ግጥሞች ጉድለት ይታይባቸዋል፤ የራስዎትን ስሜት ብቻ እየተከተሉ ስለሚጽፉ በሌላው ውስጥ ጠልቆ የመግባት ሀይል ያጥራቸዋል፤ ለምን እንደ አጣርና እንደ ሰነኢ አይጽፉም” አለው፡፡
 ሩሚም “እስቲ እንዴት አድርጌ ልጻፍ?” በማለት ጠየቀው፡፡
 ሑሳሙዲንም “ከልዩ ልዩ ምንጮች የተገኙ እውነተኛ ታሪኮችን፣ ተረቶችን፣ ምሳሌዎችን፣ ተምሳሌቶችን፣ ወዘተ… እያሰናሰሉ ቢቀላቅሉባቸውና የግጥሞቹ አካላት ቢያደርጓቸው የምን ጊዜም ተወዳጅ ይሆናሉ” ብሎ መለሰለት፡፡
 የሑሳሙዲን ምክር በሩሚ ልብ ውስጥ ጠልቆ ገባ፡፡ ከዚያም ቅኔ ሲመጣለት መቀኘት ጀመረ፡፡ ሑሳሙዲንም ከሩሚ አንደበት የሚወጣውን መጻፉን ተያያዘው፡፡ ሁለቱ ሰዎች እንዲህ እያደረጉ ዛሬ ዓለም በሙሉ የሚደመምበትን “መስነቪ”ን አስገኙ (የመጽሐፉ ትክክለኛ ስም “መሥነዊ” ነበር፤ ይህም “መሥን” ከተሰኘው የዐረብኛ ግስ የተገኘ ነው፡፡ ነገር ግን የ“ሠ” እና የ“ወ” ድምጾች በፋርሲ ቋንቋ ውስጥ ስለሌሉ ኢራናዊያን “መስነቪ” እያሉ ይጠሩታል፤ የዓለም ህዝብም የነርሱን ፈለግ በመከተል “መስነቪ” ይለዋል)፡፡
*****
ሩሚ “መስነቪ”ን የደረሰው ከዛሬ 800 ዓመት በፊት ነው፡፡ ይሁንና ዛሬም ድረስ የህዝብ ፍቅር ሳይነፈገው እንደተወደደ አለ፡፡ በዘመናችን “ሩሚ”ን እጅግ ተነባቢ ከሆኑ አስር ምርጥ ገጣሚዎች ተርታ ያሰለፈውም “መስነቪ” ነው፡፡ ይህ ዝነኛ የግጥም ድርሳን ለዓለም ስነ-ጽሑፍ መዳበር ያደረገውን አስተዋጽኦ በመመዘን የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት የአውሮፓዊያኑ 2007 በዓለም አቀፍ ደረጃ የሩሚ ዓመት ተብሎ እንዲጠራ ወስኗል፡፡ በዚያው ዓመት ሩሚ የተወለደበት ስምንት መቶኛ ዓመት ተከብሯል፡፡
የመስነቪ ይዘት ሰፊ ነው፡፡ የሰውን ልጅ አዕምሮ ያመራምራል፡፡ በዚህ ትንሽ መጣጥፍ ስለርሱ ብዙ ማውራት አይቻልም፡፡ ዳሩ ግን ከመስነቪ የተቀዳ አንድ ውብ ታሪክ ላካፍላችሁ እችላለሁ፡፡ ሩሚ ታሪኩን በግጥም ነው የጻፈው፡፡ ነገር ግን ተርጓሚው በስድ-ንባብ መልሶ ጽፎታል፡፡ እኔም በስድ ንባብ የተጻፈውን ታሪክ ነው የምጋብዛችሁ፡፡
===አራቱ ሰዎችና መንገደኛው===
  አራት ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚያም ሰዎች ግሪክ፣ ፋርሲ (ኢራናዊ)፣ ዐረብ እና ቱርክ ነበሩ፡፡ የሚፈልጉትን ነገር ይገዙበትም ዘንድ የተወሰነ ገንዘብ ተሰጣቸው፡፡ ግሪኩ “እኔ ስታፊል አምሮኛል፤ ስታፊል ግዙልንና እንብላው” አለ፡፡
ፋርሲው “የምን ስታፊል? ኡዙም ግዙልን እንጂ ሰዎች” አለ፡፡
ዐረቡ “አረ ወደዚያ! ኢነብ ነው የምንገዛው፤ ኢነብ መግዛት አለብን” በማለት ተናገረ፡፡
ቱርኩ “እንዴ! አንጉር ነው መግዛት ያለብን፤ አንጉር እንጂ ሌላ ነገር አትግዙብን” አለ፡፡
    አራቱ ሰዎች ተከራከሩ፡፡ ተነታረኩ፡፡ በጭራሽ ሊግባቡ አልቻሉም፡፡ እንዲህ እየተወዛገቡ ሳለም አንድ መንገደኛ መጣ፡፡ “ምንድነው የሚያጨቃጭቃችሁ?” በማለት ጠየቃቸው፡፡ ጉዳዩን ነገሩት፡፡ ሰውየውም “በዚህ ፍራንክ የሁላችሁንም ፍላጎት ማሟላት ይቻላል” አላቸው፡፡ ሰዎቹም “እንዴት?” በማለት ጠየቁት፡፡ ሰውዬም ገንዘቡን እንዲሰጡት ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም እንደተባለው አደረጉ፡፡
መንገደኛው ሰውዬ በአካባቢው ከነበረ የፍራፍሬ መሸጫ ገብቶ አንዱን የፍራፍሬ ዓይነት ገዝቶ ሲወጣ አራቱ ሰዎች ተያዩ፡፡ በዚያው በሳቅ ፈረሱ፡፡ ለካስ አራቱም የአንዱን ፈራፍሬ ስም በየቋንቋቸው እየጠሩት ነበር? አራቱም “ወይን እፈልጋለሁ” እያሉ ነበር የሚከራከሩት::
*****
የታሪኩን “ማዕና” (መልዕክት) አገኛችሁት አይደል? ለኛም እንደ መንገደኛው ሰውዬ ያለ አስታራቂ ይላክልን፡፡ አንድ ውጥንና ግብ ያላቸው ሰዎች ዕድሜ ልካቸውን በአተገባበር ላይ ሲጣሉ ማየትን የመሰለ አሰቃቂ ህመም የለም፡፡ ሁሉም እይታውን ቢያስተካክል መግባባት ይቻላል፡፡ ሩሚ ይህንን ነው የመከረን፡፡
ብራቮ ጀላሉዲን ሩሚ! ብራቮ መሥነቪ!
*****
የካቲት 24/2006
*****
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—-
“የማይረሱ የፕሬስ ውጤቶች” በሚል ርዕስ አንድ ጽሑፍ አቅርቤ ነበረ፡፡ በዚያ ጽሑፍ በመንግሥት ሲታተሙ የነበሩትን ጋዜጦችና መጽሔቶችን ነበር የዳሰስነው፡፡ በዚህኛው ክፍል ደግሞ በግል አሳታሚዎች አማካኝነት ሲታተሙ የነበሩትን መጽሔቶች እንዳስሳለን፡፡ ታዲያ በግል የተመሰረቱት የፕሬስ ውጤቶች እጅግ በርካታ በመሆናቸው ሁሉንም ማዳረስ አንችልም፡፡ ስለዚህ ታዋቂ የሆኑትን ብቻ  እንጠቃቅስና የቀረ ነገር ካለ ወደፊት እንመለስበታለን፡፡
1.       “ኢትዮጵያን ኦብሰርቨር” እና “አዲስ ሪፖርተር” መጽሔቶች
በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመነ-መንግሥት በእንግሊዝኛ ይወጡ የነበሩ መጽሔቶች ናቸው፡፡ መጽሔቶቹን ሲያነቡ የነበሩ ሰዎች በይዘታቸውም ሆነ በስነ-ጽሑፋዊ ውበታቸው በጣም ያደንቋቸዋል፡፡ በመጽሔቶቹ ላይ ይጽፉ ከነበሩት ጸሐፍት መካከል አብዬ መንግሥቱ ለማ እና ዳኛቸው ወርቁ ይጠቀሳሉ፡፡
2.     “መነን” መጽሔት
1950ዎቹ መጨረሻ እስከ 1960ዎቹ መጀመሪያ ድረስ ይታተም የነበረ የአማርኛ መጽሔት ነው፡፡ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ በዓሉ ግርማ ሲሆን ስብሐት ገ/እግዚአብሄርን ጨምሮ ሌሎች ታዋቂ ጸሐፍት ይሳተፉበት ነበር፡፡
3.     “ጸደይ” መጽሔት
የየካቲት 1966 የአብዮት ፍንዳታን ተከትሎ የተመሰረተ የግል መጽሔት ነው፡፡ መጽሔቱ በዘመኑ የሶሻሊስት ርዕዮተ-ዓለም ትንተና እና በማህበራዊና ኪነ-ጥበባዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው፡፡ በተጨማሪም ለየት ያሉ ኩነቶችን በ“ካርቱን” ስዕል ማሳየት የጀመረው እርሱ ይመስለኛል (እርግጠኛ አይደለሁም)፡፡
 “ጸደይ” የዘመኑ መንግሥት ከሚከተለው የፖለቲካ መስመር አኳያ የተቃኘ ነው፡፡ በመሆኑም በዚያ ዘመን የነበሩ በርካታ አንባቢያን “ጸደይ”ን በአድርባይነት ይተቹታል፡፡ ሆኖም መጽሔቱ እስከ አሁን ድረስ በተወዳጅነታቸው የሚጠቀሱ ጽሑፎችንም አስተናግዷል፡፡ ለምሳሌ ጋሼ ስብሐት ስለ“አጋፋሪ እንደሻው” መጻፍ የጀመረው በዚያ መጽሔት ላይ ነው፡፡ “ዔሊን ድንጋይ ያለበስክ” የሚለው አጭር ወግም በዚሁ መጽሔት ላይ መውጣቱን አስታውሳለሁ (እኔ የዚያ ዘመን አንባቢ አይደለሁም፡፡ አሁን የምላችሁን ጽሑፍ ያነበብኩት በ1980ዎቹ ውስጥ ነው)፡፡
4.     “ጎህ መጽሔት”      
የርዕዮተ-ዓለም ይዘት ያላቸውን ጽሑፎች ነው የሚያስተናግደው፡፡ ይሁንና የፖለቲካ መስመሩ በዘመኑ ታዋቂ ከነበረውና “ኢህአፓ” ከተሰኘው ህቡእ ፓርቲ አኳያ የተቃኘ ነው፡፡ በመሆኑም “ጎህ” በህትመት ብዙ መሰንበት አልቻለም (ህትመቱ ከሶስት እትሞች በኋላ የተቋረጠ ይመስለኛል)፡፡
ታዲያ “ጎህ” በዚያች ትንሽ ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ መነጋገሪያ ለመሆን በቅቷል፡፡ በተለይም የጆሴፍ ስታሊን የህይወት ታሪክ በማስመልከት በጸደይ መጽሔት ላይ በወጣ ጊዜ ጎሕ መጽሔት ጽሑፉን በመቃወም ስታሊንን እየወቀሰ የሰጠው ምላሽ ከጸደይ ጋር ጦርነት ውስጥ ከትቶት ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ የጸደይ መጽሔት ጸሐፊዎች ጎህን “አናርኪስት” እስከማለት ደርሰዋል፡፡
በጎህ መጽሔት ላይ ይጽፉ ከነበሩት ታዋቂ ሰዎች አንዱ የኢህአፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የነበረው ዮሐንስ ብርሃኔ ነው (ዮሐንስ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አስተማሪ የነበረ ሲሆን በመጋቢት ወር 1969 በአቃቂ ኬላ ላይ ተገድሏል)፡፡ በነገራችን ላይ ጎሕ ከደርግ መንግሥት ውድቀት በኋላ በ1984 መጨረሻ ላይ እንደገና መውጣት ጀምሮ ነበር፡፡ ነገር ግን በገበያ ውስጥ ብዙም ሊቆይ አልቻለም፡፡ ከዚያም ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ (በ1993) “ጎህ” የተሰኘ መጽሔት ተጀምሯል፡፡ ሆኖም ይህኛውም መጽሔት ከሁለት ዓመታት ቆይታ በኋላ ተዘግቷል፡፡
5.     “ቢላል”
በኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጉዳይ ላይ በማተኮር የሚዘጋጅ ሲሆን በ1966 የአብዮት ፍንዳታ ወቅት ነው መታተም የጀመረው፡፡ ነገር ግን ከሁለት እትም በላይ ሳይራመድ ጠፋ፡፡ ከአስራ አራት ዓመታት በኋላ በመስከረም ወር 1985 በዚሁ ስም አዲስ መጽሔት መዘጋጀት ጀመረ፡፡ ይሁንና የኋለኛው “ቢላል” ከድሮው ጋር ተመሳሳይ ስያሜ ከመያዙ ውጭ አሳታሚያቸው አንድ አይደለም (የ1985ቱ “ቢላል” በነጃሺ አሳታሚ አማካኝነት ነበር የሚዘጋጀው)፡፡
ከሁለቱ “ቢላል” መጽሔቶች መካከል በአንባቢያን ዘንድ ልዩ ትውስታን ጥሎ ያለፈው የ1985ቱ “ቢላል” ነው፡፡ የዚህ መጽሔት ዋና አዘጋጅ ታዋቂው የኢትዮጵያ የእስልምና ሊቅ ሐጂ ሙሐመድ ወሌ ነበሩ፡፡ በ1987 በአንዋር መስጊድ ረብሻ ሲነሳ የ“ቢላል”ም ህትመት ተቋርጧል፡፡
6.     “እፎይታ”
በ1984 የፕሬስ አዋጅ ሲታወጅ ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመው የግል መጽሔት “እፎይታ” ነው፡፡ አሳታሚው “ፋና ዴሞክራሲ አሳታሚ” ይባላል፡፡ ለረጅም ጊዜ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ያገለገለው ደግሞ ተስፋዬ ገብረአብ ነው (ተስፋዬ በመጽሔቱ ላይ በአዘጋጅነት የተጠቀሰው “ዋለልኝ ብርሃነ” በሚል ስም ነበር)፡፡ ይሁንና መጽሄቱ “ነጻ ነኝ” ቢልም አብዛኛው አንባቢ የኢህአዴግ ልሳን ይለው ነበር፡፡ በእርግጥም መጽሔቱ የኢህአዴግ መስመር ተከታይ እንደነበረ ከጽሑፎቹ መረዳት ይቻላል፡፡ ተስፋዬ ገብረአብ ባሳተመው የጋዜጠኛው ማስታወሻም ይህንኑ አምኖ ነበር፡፡ የኢህአዴግ አባላት መጽሔቱን በትዕዛዝ ይገዙት የነበረ መሆኑም ሌላው አስረጂ ነው፡፡
   “እፎይታ” መታተም ሲጀምር በደርግ ዘመን በተፈጸሙ የቀይ ሽብር ወንጀሎች፣ በዓለም አቀፍ ጉዳዮችና በኪነ-ጥበባት ጉዳዮች ላይ ስለሚያተኩር  በርካታ አንባቢያን ነበሩት፡፡ በዝግጅቱም የሺጥላ ኮከብ፣ ደረጄ ደስታ፤ ስብሐት ገብረ እግዚአብሄር እና አረፈዓይኔ ሐጎስን የመሳሰሉ ደራሲዎችና ጋዜጠኞች ይሳተፉ ነበር፡፡ በመጽሔቱ የታተሙ በርካታ መጣጥፎችና አጫጭር ልብ-ወለዶች “እፍታ” በተሰኙት ተከታታይ መድብሎች ተሰባስበዋል፡፡
 
“እፎይታ” ከ1987 በኋላ ድሮ በነበረበት ይዘት መቀጠል አልቻለም፡፡ በመሆኑም የአንባቢዎቹ ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ ቀንሷል፡፡ ቢሆንም በመንግሥታዊዎቹ “አዲስ ዘመን” እና “ኢቴቪ” የማይዘገቡ ወቅታዊ ጉዳዮችን በብቸኝነት እንዲያስተናግድ ስለሚደረግ እስከወዲያኛው ድረስ በአንባቢ እጦት ድርቅ አልተመታም፡፡
7.     “ሩሕ”
“ዩሬካ” በሚባል አሳታሚ ድርጅት አማካኝነት በሚያዚያ 1984 ነው መታተም የጀመረው፡፡ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ ጋሽ ጳውሎስ ኞኞ ነው፡፡ ሆኖም ጳውሎስ ከጥቂት እትሞች በኋላ (በ1984 ክረምት ወራት) ሞቷል፡፡
በመጽሔቱ ላይ ከሚጽፉ ብርዕተኞች መካከል “ሱልጣን ኢንሻ አላህ” የተባለው ጸሐፊ ይጠቀሳል፡፡ ይህ መጽሔት በ1985 ከተቋረጠ በኋላ በ1993 እንደገና አንሰራርቷል፡፡ ነገር ግን በዚህኛውም ጊዜ ብዙ ሳይጓዝ ተቋርጧል፡፡ “ሩሕ” መጽሔት በደንብ የሚታወሰው የሼኽ ሑሴን ጂብሪልን ትንቢታዊ ግጥሞች ለመጀመሪያ ከአንባቢያን ጋር በስፋት ያስተዋወቀ በመሆኑ ነው፡፡
8.     “ጦቢያ”
በታዋቂው ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ አማካኝነት በ1984 የተጀመረ ነው፡፡ “ጦቢያ”ን ለየት የሚያደርገው በሚያዚያ 1984 ከተጀመሩት የነጻ ፕሬስ ውጤቶች መካከል ሳይቋረጥ እስከ መስከረም 1998 ድረስ ለመጓዝ የቻለ ብቸኛ መጽሔት መሆኑ ነው፡፡ በመጽሔቱ ላይ ይጽፉ ከነበሩት ብዕርተኞች መካከል ጸጋዬ ገብረመድህን አርአያ፣ ስንሻው ተገኘ እና ሐሰን ዑመር አብደላ በጣም ይታወሳሉ፡፡
በጦቢያ መጽሔት ከወጡት ጽሑፎች መካከልም ዶ/ር መረራ ጉዲና በኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ዙሪያ የጻፏቸው ተከታታይ ጽሑፎችና በ1953ቱ የታህሳስ ግርግር ዙሪያ የተጠናቀረው ታሪካዊ ዘገባ ይጠቀሳሉ፡፡ በ1987 አጋማሽ ላይ በጄኔቭ የኢትዮጵያ አምባሳደር ከነበሩት ጓድ ካሳ ከበደ ጋር የተደረገው ቃለ-መጠይቅም የመጽሔቱን ተፈላጊነት በእጅጉ አንሮት ነበር፡፡ 
9.     “ሳሌም”
በኢትዮጵያ ታሪክ ከተከሰቱ የምንጊዜም ተወዳጅ መጽሔቶች አንዱ ነው፡፡ “ሳሌም” በአቀራረቡ ሚዛናዊ በመሆኑ በርካታ ደንበኞች ነበሩት፡፡ እንዲሁም ለግል መጽሔቶች ባልተለመደ ሁኔታ የትኛውንም አካል አነጋግሮ ዘገባ ይሰራ ነበር፡፡ የመንግሥት ባለስልጣናት ለሳሌም መረጃና ቃለ-መጠይቅ ይሰጡ ነበር፡፡ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችም እንደዚያው!!
ሳሌም መጽሔት በአንባቢያን ዘንድ በጣም የሚታወሰው በሁለት ነገሮች ነው፡፡ አንደኛው በወሩ ውስጥ አነጋጋሪ በሆነ ጉዳይ ዙሪያ የግራና የቀኝ ምንጮችን እያነጋገረ የሚያቀርበው “አቢይ ርዕስ” ነው፡፡ የዚህ ዘገባ አጻጻፍ ከብዙ ዓመታት በኋላ “አዲስ ነገር” ጋዜጣ ይዞት ከመጣው “ፊቸር ጽሑፍ አጻጻፍ” ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ልዩነቱ ሳሌም መጽሔት ከዋናው ዘገባ አጠገብ ፎቶግራፎችንና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የተደረጉ አጫጭር ቃለ-ምልልሶችን የሚያክል መሆኑ ነው፡፡
  በሌላ በኩል ሳሌም መጽሔት ታዋቂ የፖለቲካ ሰዎችን፣ ምሁራንንና አርቲስቶችን እየጋበዘ በሚሰራቸው ልዩ ቃለ-መጠይቆችም ይታወሳል፡፡ ሳሌም ካስተናገዳቸው ቃለ-መጠይቆች መካከል የኦነግ ም/ሊቀመንበር ከነበሩት አቶ ሌንጮ ለታ፣ ከቀድሞው የደህንነት ሚኒስትር ኮ/ል ተስፋዬ ወልደሥላሤ፣ ከቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ፍቅረ ሥላሤ ወግደረስ፣ የደርግ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከነበሩት ኮ/ል ደበላ ዲንሳና ዶ/ር ዓለሙ አበበ እንዲሁም ከአርቲስት ሙሉቀን መለሠ ጋር የተደረጉት ይጠቀሳሉ፡፡ “ሳሌም” በ1986 መጨረሻ ላይ ለጊዜው ባላወቅኩት ምክንያት ተዘግቷል፡፡ በመጽሔቱ ላይ በዘጋቢነት ይሰሩ ከነበሩት መካከል የአሁኑ አርቲስት ሰይፉ ፋንታሁን ይጠቀሳል፡፡
10.    “አሌፍ”
1985/86 ከሳሌም ቀጥሎ ሰፊ ተነባቢነት የነበረው መጽሔት ነው፡፡ በአቀራረቡም ከሳሌም ጋር የመመሳሰል ነገር ይታይበት ነበር፡፡ በተለይ የመጽሔቱ “ዐቢይ ርዕስ” አጠር ከማለቱ በስተቀር ከሳሌም የ“ፊቸር ዘገባ” ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ በአሌፍ የሚታየው የተለየ ነገር ቢኖር ከዋናው ዘገባ አጠገብ ከርዕሱ ጋር የሚሄዱ አነጋጋሪ ጽሑፎችን የሚያክል መሆኑ ነው፡፡
የአሌፍ መጽሔት ባለቤት አቶ ብርሃነ መዋ ነበሩ፡፡ ዋና አዘጋጁ ደግሞ አሁን የቪ.ኦ.ኤ ዘጋቢ ሆኖ የሚሰራው መለስካቸው አመሀ ነው፡፡ በዘጋቢነት (ሪፓርተርነት) ይሰሩ ከነበሩት መካከልም አሁን የሸገር ኤፍ.ኤም ታዋቂ ሰው የሆነችው ጋዜጠኛ መአዛ ብሩ ትጠቀሳለች፡፡
ይህ መጽሄት ስለኢህአፓ ጉዳይ እየደጋገመ ይጽፍ ነበር፡፡ በ1986 ለመዘጋት የበቃው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡
11.     “ሪፖርተር” መጽሔት
የአማረ አረጋዊ ኩባኒያ በሆነው ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ሴንተር የሚዘጋጅ ወርሃዊ መጽሔት ነበረ፡፡ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ እሸቴ አሰፋ  ሲሆን ከመጽሔቱ ከፍተኛ አዘጋጆች መካከል ኋላ ላይ የአዲስ ነገር ጋዜጣ ማኔጂንግ ኤዲተር የሆነው መስፍን ነጋሽ ይጠቀሳል፡፡
 ሪፖርተር በመጽሔትነቱ ከሪፖርተር ጋዜጣ በጣም ይለያል፡፡ ሪፖርተር ጋዜጣ ብዙ ገጽ ቢኖረውም አብዛኛው ክፍል በማስታወቂያ የተያዘ ነው፡፡ የንባብ ጥማት ላለው ሰው ብዙም አርኪ የሚባል አይደለም፡፡ ሪፖርተር መጽሔት ግን በመረጃና በምርምር የተደገፉ አነጋጋሪ፣ አከራካሪ እና አወያይ ጽሑፎችን ይዞ ይወጣ ስለነበረ በተለይም በምሁሩ ክፍል ከፍተኛ ተነባቢነት ነበረው፡፡ በሪፖርተር መጽሔት ከወጡ ጽሑፎች መካከል ኤርትራ “ናቅፋ” የተባለውን ገንዘብ በስራ ላይ ባዋለችበት ወቅት የተጠናቀረው ዘገባ፣ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በፈነዳበት ጊዜ የተጠናቀረ ዘገባ፣ እነ ተወልደ ወልደማሪያም ከህወሐት ተገንጥለው በወጡበት ወቅት “ቦናፓርቲዝም” በሚል ርዕስ የወጣው አነጋጋሪ ዘገባ፣ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ከኦህዴድ በወጡበት ጊዜ የተጠናቀረው ቃለ-ምልልስ፣ በጋምቤላው ግጭት ዙሪያ የተጠናቀረው ሪፖርታዥ በከፍተኛ ደረጃ ተነበዋል፡፡ በመጽሔቱ ላይ መጣጥፎችን ከሚያቀርቡ ብዕርተኞች መካከል የኢህዴን/ብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የነበረው መዝሙር ፈንቴ ይጠቀሳል፡፡
ሪፖርተር እስከ 1997 መግቢያ ድረስ በህትመት ላይ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡ መጽሔቱ መቼ እንደተቋረጠና በምን ምክንያት እንደተቋረጠ ግን ትክክለኛ መረጃ የለኝም፡፡
12.     “ኢትኦጵ”
በሰኔ ወር 1991 የተጀመረ የግል መጽሔት ነው፡፡ መጽሔቱ በተለይ በመረጃ ስፋትና ጠለቅ ባለ ትንታኔው ይታወሳል፡፡ ታሪክ-ነክ ጉዳዮችንም እየቆሰቆሰ ብዙ አንባቢያንን በማፍራቱም ይታወቃል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በብርቱ የተቋሰሉ ታዋቂ የፖለቲካ ሰዎች ይጽፉበት ስለነበረ ከፍተኛ ተፈላጊነት ነበረው፡፡ ለምሳሌ እነ አቶ እያሱ አለማየሁ፣ አቶ አሰፋ ጫቦ፣ አቶ አብርሃም ያየህ፣ አቶ ጌታቸው ጋረደው የመሳሰሉት የፖለቲካ ሰዎች በርካታ ጽሑፎቻቸውን አቅርበውበታል፡፡ የገጣሚ ሀይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው) እና የህወሐት ቁልፍ ሰው የነበረው የብስራት አማረ (ከኮሎምበስ-ኦሃዮ) ተከታታይ ጽሑፎችም ተስተናግደውበታል፡፡
በሌላ በኩል “ኢትኦጵ” መጽሔት በህትመት ኢንዱስትሪው የሚታወስበት አንድ ታሪክ አለው፡፡ ይህም ታዋቂና ዝነኞች ብቻ የመጽሔት እንግዳ የሚደረጉበትን ልማድ በመስበር በዝቅተኛ ኑሮ ውስጥ ለሚገኙት የህብረተሰብ ክፍሎች ቃለ-መጠይቅ የማድረግ ልማድን ማስተዋወቁ ነው፡፡ እነዚህ ቃለ-መጠይቆች “መንገድ” በተሰኘው አምድ ይስተናገዱ ነበር (እኔ ኢትኦጵን ማንበብ የምጀምረው “መንገድ” ከተሰኘው ዓምድ ነበረ)፡፡ “ኢትኦጵ” ከምርጫ 1997 ግርግር ጋር በተያያዘ በመስከረም ወር 1998 ተዘግቷል፡፡
13.    “አዲስ ጉዳይ”
ይህ መጽሔት በ1998 ገደማ ሲጀመር “ሮዝ” የሚል ስም ነው የነበረው፡፡ በ2003 ደግሞ “አዲስ ጉዳይ” የሚለውን ስያሜ ያዘ፡፡መጽሔቱ በጅምሩ ላይ በኪነ-ጥበብና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ያተኩር ነበር፡፡ “አዲስ ጉዳይ” በሚል ስም መዘጋጀት ከጀመረ በኋላ ግን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያው ጉዳዮችን ጨምሮ ሁሉንም ዘርፎች የሚዳስስ ሆኗል፡፡ በመጽሄቱ ላይ ስም ያላቸው ምሁራንና ታዋቂ ወጣት ጸሐፍት የሚሳተፉ ከመሆናቸው የተነሳ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሰፊ አንባቢያንን ለማፍራት በቅቷል፡፡ “አዲስ ጉዳይ” የሚታወስበት ሌላኛው ነገር ደግሞ መጽሔቶች በወር ብቻ የሚዘጋጁበትን የረጅም ጊዜ ልማድ ሰብሮ የአስራ አምስት ቀን እና ሳምንታዊ ህትመትን ማስተዋወቁ ነው፡፡
*****
ከላይ ከጠቀስኳቸው መጽሔቶች በተጨማሪ መስታወት፣ ማለዳ፣ አእምሮ፣ አቢሲኒያ፣ ሉሲ፣ ገዳ፣ የአፍሪካ ቀንድ፣ ህብር፣ ለዛ፣ ምኒልክ፣ ልሳነ-ህዝብ፣ ኮከብ፣ ማሕሌት፣ ዜጋ፣ ወዘተ… የተባሉ መጽሔቶችም በሀገራችን ይታተሙ ነበር፡፡ አሁን ግን አንዳቸውም የሉም፡፡ በህትመት ላይ ካሉት መጽሔቶች መካከል ዘላቂ በሆነ መልኩ የሚቀጥሉት የትኞቹ ናቸው?… ወደፊት አብረን የምናየው ይሆናል፡፡ እድሜና ጤና ይስጠንና!!
—-
ነሐሴ 11/2006
አፈንዲ ሙተቂ
—-
Afendi Muteki is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—-
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሲጠቀሱ በቅድሚያ የሚታወሱት በላስታ አውራጃ፣ በ“ሮሃ” (ላሊበላ) ከተማ አጠገብ ከአንድ-ወጥ ድንጋይ ተፈልፍለው የተሰሩት አስራ አንድ ቤተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ የአስራ አንዱ ቤተ ክርስቲያናት ስም እንደሚከተለው ነው፡፡
1.      ቤተ መድኃኒ-ዓለም
2.     ቤተ ማርያም
3.     ቤተ ደናግል
4.     ቤተ መስቀል
5.     ቤተ ሚካኤል
6.     ቤተ ጎለጎታ
7.     ቤተ አማኑኤል
8.     ቤተ ገብርኤል
9.     ቤተ አባ ሊባኖስ
10.    ቤተ መርቆሬዎስ
11.     ቤተ ጊዮርጊስ
እነዚህ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙት በሦሥት የተለያዩ ስፍራዎች ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ስድስቱ በአንድ ስፍራ፣ ተከታዮቹ አራቱም በሌላ ስፍራ ላይ ነው የተሰሩት፡፡ ቤተ ጊዮርጊስ ግን ከሁሉም ተነጥሎ ለብቻው ቆሟል፡፡ ከአብያተ ክርስቲያናቱ ውስጥ ትልቁ “ቤተ መድኃኒ-ዓለም” ሲሆን በኪነ-ህንጻውና በዲዛይኑ በዓለም ዙሪያ የተደነቀው ግን በመስቀል ቅርጽ የተሰራው “ቤተ ጊዮርጊስ” ነው፡፡
እነዚህን ቤተ ክርስቲያናት ያሳነጸው ከ1181-1221 የነገሠው የዛግዌው ንጉሥ ገብረ መስቀል ሲሆን ይህ ንጉሥ በታሪክ ምዕራፎች በደንብ የሚታወቀው “ላሊበላ” በሚል ስም ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ለንጉሥ ላሊበላ የቅድስና ማዕረግ መስጠቷ ይታወቃል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (UNESCO) በበኩሉ የላሊበላ አብያተ ክርስቲያናትን በዓለም ቅርስነት መዝገቦአቸዋል፡፡
       *****
በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስትና ደንብና ትውፊት መሰረት አንድ ቤተ-ክርስቲያን የሚታነጸው ሦሥት ክፍሎች እንዲኖሩት ተደርጎ ነው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል “መቅደስ” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ታቦት (ጽላት) በዚህ ክፍል ውስጥ ነው የሚቀመጠው፡፡ በመቅደሱ ውስጥ እንዲገቡ የሚፈቅድላቸውም ካህናት ብቻ ናቸው፡፡ ሁለተኛው ክፍል “ቅድስት” ይባላል፡፡ የ“ስጋ ወደሙ” ስርዓት የሚፈጸመው በዚህኛው ክፍል ውስጥ ነው፡፡ ሶስተኛው ክፍል “ቅኔ ማህሌት” ነው፡፡ በዚህ ክፍል ውስጥ በአንድ ወገን ደብተሮች ይዘምራሉ፡፡ በሌላ ወገን ቀሳውስት ሰዓታት ይቆማሉ፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ የሚመጡት ምእመናንም ስርዓተ ቅዳሴውንና ልዩ ልዩ ስብከቶችን የሚከታተሉት በዚህ ክፍል ውስጥ ነው፡፡
       *****
በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክህነት ስር የሚተዳደሩት አብያተ-ክርስቲያናት በሶስት ይከፈላሉ፡፡ እነዚህም ገዳም፣ ደብር እና “ገጠር” (አጥቢያ) በመባል ይታወቃሉ፡፡ “ገዳም” የሚባለው መነኮሳት ከዓለማዊ ኑሮ ተገልገለው የምንኩስና ህይወት የሚኖሩበት ቤተ-ክርስቲያን ነው፡፡ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን ገዳም የቆረቆሩት በ5ኛው ክፍለ ዘመን ወደ ኢትዮጵያ የመጡት ሶሪያዊው “አቡነ-አረጋዊ” ሲሆኑ በርሳቸው የተቆረቆረውም በትግራይ የሚገኘው የ“ደብረ ዳሞ” ገዳም ነው፡፡ ሌሎች ታዋቂ ገዳማት ደግሞ “ደብረ-ሊባኖስ” (በሰሜን ሸዋ፣ ሰላሌ አውራጃ ውስጥ የሚገኝ፣ በአስራ ሦሥተኛው ክፍለ ዘመን በኖሩት “አቡነ ተክለ-ሃይማኖት” የተመሰረተ)፣ “ደብረ ቢዘን” (በደቡብ ኤርትራ፣ ሰራዬ አውራጃ ውስጥ የሚገኝ፣ በአስራ አራተኛው ክፍለ ዘመን በኖሩት “አባ ኤዎስጣቴዎስ” የተመሰረተ)፣ “ደብረ ወገግ” ወይንም የ“አሰቦት ገዳም” (በሀረርጌ ክፍለ ሀገር፣ በአሰቦት ተራራ ላይ የሚገኝ፤ “አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ” በተባሉት ታዋቂ መነኩሴና የብዙ መጻሕፍት ደራሲ እንደተመሰረተ የሚታመን) እና የ“ዋልድባ ገዳም” (በትግራይና ጎንደር ወሰን ላይ የሚገኝ፤ “አባ ሳሙኤል” በተባሉ መነኩሴ በአስራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን የተመሰረተ) የመሳሰሉት ናቸው፡፡ የገዳም አስተዳዳሪ ከመነኮሳቱ መካከል በዕድሜው፣ በስነ-ምግባሩ፣ በዕውቀቱ እና በገድሉ ተመርጦ “አባት” በሚል ማዕረግ ይሾማል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት “ደብር” ይባላሉ፡፡ እነዚህኛዎቹ በርከት ያለ ህዝብ በሚኖርበት ስፍራ የተሰሩ እና ሁለገብ የቤተ-ክርስቲያን አገልግሎት የሚሰጡ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ ቆየት ባለው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ትውፊት መሰረት ደብሮች የሚሰሩት በኮረብታ ላይ ነው፡፡ ደብሮቹ የሚጠሩትም በክርስትና ታሪክ ቅዱስ መሆናቸው በተመሰከረላቸው ቀደምት የሃይማኖት አባቶች፣ በሰማእታትና በመላዕክት ስም ነው፡፡
   የደብር አስተዳዳሪ “አለቃ” ይባላል፡፡ ሆኖም እንደ አስፈላጊነቱ “ንቡረ እድ”፣ “ሊቀ-ስልጣናት”፣ “መልአከ ጸሐይ”፣ “መልአከ ገነት” ወዘተ… በመሳሰሉ ማዕረጎችም ሊጠራ ይችላል፡፡ አንዳንድ ደብሮች በየዓመቱ የሚከናወኑ ታላላቅ የንግሥ በዓላትን በማስተናገድ ይታወቃሉ፡፡ በዚህ ረገድ ጎላ ብለው የሚጠቀሱት የአክሱም ጽዮን ማሪያም ቤተ-ክርስቲያን፣ የግሸን ማሪያም ቤተ-ክርስቲያን እና የቁልቢ ገብርኤል ቤተ-ክርስቲያን ናቸው፡፡
“ገጠር” የሚባሉት በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የሚሰሩ ቤተ-ክርስቲያናት ናቸው፡፡ እነዚህ ቤተ-ክርስቲያናት መንፈሳዊ አገልግሎት የሚሰጡት  ቅዳሜና እሁድ ብቻ ነው፡፡ የገጠር ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ “መሪ ጌታ”፣ “ጎበዝ” እና “አለቃ” በሚሉ ማዕረጎች ይጠራል፡፡
       *****
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ስርዓት መሰረት ዘጠኝ ዐቢይ በዓላት፣ ዘጠኝ ንዑሳን በዓላትና ሰባት አጽዋማት አሉ፡፡ ዐቢይ በዓላት የሚባሉት “ልደት” (ገና)፣ “ጥምቀት”፣ “ደብረ ታቦር”፣ “ሆሳዕና”፣ “ስቅለት”፣ “ትንሳኤ”፣ “ዕርገት” እና “ጰራቅሊጦስ” ናቸው፡፡ ንዑሳን በዓላት የሚባሉት ደግሞ “መስቀል”፣ “ስብከት”፣ “ብርሃን”፣ “ኖላዊ”፣ “ግዝረት”፣ “ልደተ ስምዖን”፣ “ቃና ዘገሊላ”፣ “ደብረ ዘይት” እና “ሁለተኛው መስቀል” (መጋቢት አስር ቀን የሚውል) ናቸው፡፡
ሰባቱ አጽዋማት “ዐቢይ ጾም” (ሁዳዴ)፣ “ጾመ ሐዋሪያት”፣ “ጾመ ፍልሰታ”፣ “ጾመ -ነቢያት”፣ “ገሃድ”፣ “ጾመ ነነዌ” እና የ“ረቡዕ እና ዐርብ” ጾም ናቸው፡፡ የእምነቱ ተከታዮች ከቻሉ ሁሉንም አጽዋማት ይጾማሉ፡፡ ካልቻሉ ግን “ዐቢይ ጾም”ን፣ “ጾመ-ፍልሰታ”ን እና ረቡዕና ዐርብን የመጾም ግዴታ አለባቸው፡፡
       *****
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 5/2007
በገለምሶ ከተማ ተጻፈ፡፡
ምንጮች
1.      ሉሌ መልአኩ፡ “የቤተ ክርስቲያን ታሪክ”፡ ትንሳኤ ብርሃን አሳታሚ ድርጅት፤ 1986
2.     ተክለ-ጻዲቅ መኩሪያ፡ የኢትዮጵያ ታሪክ ከአጼ ልብነ-ድንግል እስከ አጼ ቴዎድሮስ፣ 1936
3.     Encyclopaedia Ethiopica: University of Hamburg: 2004: Volume 1-5
4.      የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ድረ-ገጽ (www.ethiopianorthodox.org )


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
 እውነቴን ነው፡፡ በእጅጉ ላያቸው ከምጓጓላቸው የሀገራችን አካባቢዎች አንዱ ትግራይ ነው፡፡ ሰሜናዊው የኢትዮጵያ ዋልታ! የውበትና የድምቀት መዘክር!
ትግራይ የመንግሥተ-አክሱም ሀገር! የሳባ ፊደል ጥንስስ! የግዕዝ ልሳን ውርስ! የዳማት ታሪክ መስተንክር! በአህጉረ አፍሪቃ የመጀመሪያው ሳንቲም የተወቀረበት የስልጣኔ ጥንስስ!
ትግራይ! የኤዛና ሀገር! የሳይዛና ሀገር! የካሌብ ሀገር! የአብርሃ ወአጽብሃ ሀገር! የአሕመድ አል-ነጃሺ ሀገር! የአንበሳ ውድም ሀገር! የአጼ ዮሐንስ አራተኛ ሀገር፣ የነገሥታት ዙፋን መቀመጫ!
ትግራይ የአሉላ ሀገር! የስሁል ሚካኤል ሀገር! የሰበጋዲስ ሀገር! የመንገሻ ዮሐንስ ሀገር! የበሻይ አውአሎም ሀገር! የቀዳማይ ወያኔ ሀገር! የኃየሎም አርአያ ሀገር! የሌሎችም ጀግኖችና አርበኞች መፍለቂያ!
ትግራይ የጥላሁን ግዛው ሀገር! የብርሃነ መስቀል ረዳ ሀገር! የዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ሀገር! የዘርዑ ክህሸን ሀገር! የብርሃነ እያሱ ሀገር! የፀሎተ ህዝቅያስ ሀገር! የዮሴፍ አዳነ ሀገር! የዶ/ር ንግስት አዳነ ሀገር! የመለስ ተክሌ ሀገር! የግደይ ገብረዋህድ ሀገር! የአረጋዊ በርሀ ሀገር! የመለስ ዜናዊ ሀገር! የአብረሃም ያየህ ሀገር! የገብረመድህን አርአያ ሀገር! የግደይ ዘርዓ ጽዮን ሀገር! የኦቦይ ስብሐት ነጋ ሀገር! የስዬ አብረሃ ሀገር! የገብሩ አስራት ሀገር! የዶ/ር ሀይሉ አርአያ ሀገር! የጓድ ፍስሐ ደስታ ሀገር! የልዑል መንገሻ ስዩም ሀገር! የአብረሃ ደስታ ሀገር! ሺ ምንተሺህ ቱባ ፖለቲከኞችንና የነጻነት ፋኖዎችን ያፈራ ምድር!
ትግራይ የገብረ-ህይወት ባይከዳኝ ሀገር! የጊላወርቅ ተስፋማሪያም ሀገር! የስብሐት ገብረ-እግዚአብሄር ሀገር! የተወልደብርሃን ገብረ-እግዚአብሄር ሀገር! የአምባሳደር ካሳ ገብረ-ህይወት ሀገር! የዶ/ር ወልዳይ አምሀ ሀገር! የዶ/ር አሰፋ መድኃኔ ሀገር! ወገን ያስከበሩ ጎምቶ ምሁራን የበቀሉበት ደብር!
ትግራይ የቅዱስ ያሬድ ሀገር! የፈላስፋው ዘርዓ ያዕቆብ ሀገር! የኪሮስ አለማየሁ ሀገር! የኪሮስ ሀይለሥላሴ ሀገር! የሶፊያ አፅብሃ ሀገር! የኢያሱ በርሀ ሀገር! የብርሃነ ሀይለ ሀገር! የአብረሃም ገብረ መድህን ሀገር! የባህታ ገብረ ህይወት ሀገር! የማህሌት ገብረገርግስ ሀገር! ጥበብን እየዳመጡ የፈተሉ ከያኒያን የተገኙበት የኪነት መዘክር!
ትግራይ! የአቡነ አረጋዊ ሀገር! የሼኽ ቡሽረል ከሪም ሙስጠፋ ሀገር! የአባ ገብረ መድህን ሀገር! የአባ ሳህለ ድንግል ሀገር! የአቡነ ማቲያስ ሀገር! እልፍ አዕላፍ የሃይማኖት ሊቃውንትና ሰባኪያን የወጡበት ምድር!
ትግራይ የምሩጽ ይፍጠር ሀገር! የወርቅነሽ ኪዳኔ ሀገር! የገብረ እግዚአብሄር ገብረማሪያም ሀገር! የገብረመድህን ሀይሌ ሀገር!  ድፍን ኢትዮጵያን ያስጠሩ ውድ ስፖርተኞች የተገኙበት ሰፈር!
ትግራይ የአባዲ ጸጋዬ ሀገር፣ የዳንኤል ግደይ ሀገር፣ የግርማ በርሀ ሀገር፣ የሙሐመድ አደም ሀገር፣ የአግዘው አደራ ሀገር፣ የአግዐዚ አምሃ ሀገር፣ የተወልደ መዝገቡ ሀገር፣ የቢነጋ ተወልደ ሀገር፣ በትምህርት ቆይታዬ የማውቃቸው የበርካታ ምርጥ ጨዋና ሰላማዊ ጓደኞቼ ሀገር!
            *****
      “የማያውቁት ሀገር አይናፍቅም” ይባላል፡፡ እኔ ግን በዚህ አላምንም፡፡ የማያውቁትን ሀገር ያህል ለማየት የሚያጓጓ ነገር የለም፡፡ የሚያውቁትንማ ለምን ይጓጉለታል? ለማየት የሚናፍቀውስ የማያውቁት ሀገር ነው፡፡ ለምሳሌ እኛ ትግራይን በጽሑፍና በቪዲዮ ካልሆነ በስተቀር ለአንድም ቀን አይተናት አናውቅም፡፡ ይሁን እንጂ ስለርሷ ያነበብነውና የሰማነው ሁሉ ዘወትር እንድንናፍቃት እያደረገን ነው (“እኛ” እንደ ጃንሆይ የሀረር ልጅ ስለሆንን “እኛ” በማለታችን “ እናንተ እነማን ናችሁ?” የሚል ጥያቄ እንዳታነሱብን ከዚህ በፊት አስታውቀናችኋል)፡፡ መቼ እንደምናደርገው እርግጠኛ ሆነን መናገር ቢያስቸግረንም ትግራይን መጎብኘታችን አይቀሬ ነው፡፡ ዕድሜና ጤናውን አብዝቶ ይስጠንና!
            *****
    አምና ታዋቂው ሳክስፎኒስት ቴዎድሮስ ምትኩ ማረፉን ከዜና ማሰራጫዎች ሰምተን ነበር፡፡ እርሱን ለመዘከር በሚልም  ስራዎቹ በልዩ ልዩ ሬድዮ ጣቢያዎች ተዳስሰዋል፡፡ በተለይ በመሳሪያ ብቻ የተቀነባበረው ዝነኛ ካሴቱ በየጣቢያው እንደ ጉድ ተለቆለታል፡፡ ታዲያ ከነዚያ ስራዎች መካከል እጅግ ተደጋግመው የተሰሙት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ከነርሱም አንዱ ቴዲ የባህታ ገብረ-ህይወትን ተወዳጅ የትግርኛ ዘፈን የተጫወተበት ሙዚቃው ነው፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክም የህዝብ ፍቅር እየተቸራቸው ከዘመን ዘመን ለመሻገር ከበቁ ዜማዎች አንዱ ይህ የባህታ ገ/ህይወት ዘፈን ነው፡፡
      እውነት ነው! “ባህታ” ሲባል በብዙዎቻችን አዕምሮ ከተፍ የሚሉት ሁለት ዜማዎች ናቸው፡፡ አንደኛው የአማርኛው “ካላጣሽው አካል” ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ይህ የትግርኛ ዜማ ነው፡፡ የዚያ ዜማ ግጥምም እንደሚከተለው ነው (በነገራችን ላይ ግጥሙን በብዕራችን እንድንጨብጥ የረዳን ሙስጠፋ ሙሐመድ የተባለው የትግራይ ጓደኛችን ነው፡፡ ምስጋና ይገባዋል)፡፡
ስቓይ ይከአልዩ (3)
ሁልጊዜ…
ናይ ፍቕሪ ስቓይ ግን ዘይ ይከአልዩ
ዝደለዮ ተዘይ ረኸበ
የአማርኛ ፍቺው እንደሚከተለው መሆኑም ተነግሮናል፡፡
ስቃይ ይቻላል!
ሁልጊዜ…
የፍቅር ስቃይ ግን አይቻልም
የሚሻውን ካላገኘ በቀር
  ከትግራይ ከያኒያን ብዙ ትዝታ የጣሉብኝ ግን ሶስት ሰዎች ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ኪሮስ አለማየሁ ነው፡፡ የትግርኛ ዜማን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት ከርሱ ይመስለኛል፡፡ በተለይ “እንጓይ ፍስስ” ከልቡ መስተፋቅራዊ ውበት የነገሠበት ስራ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ በድሮው ጊዜ ዘፋኙ የሚዘፍነው ስለደስታ ይመስለኝ ነበር፡፡ የዜማው መልዕክት እኔ ከጠበቅኩት ተቃራኒ እንደሆነ የተረዳሁት አሁን በቅርቡ ነው፡፡ “እንጓይ ፍስስ” ሲባል “የአጥንቴ መቅኒ ይፍሰስ” ማለት እንደሆነ ያስረዳን የሽረ ተወላጅ የሆነው ወዳጃችን ሙስጠፋ ሙሐመድ ነው፡፡
     ሁለተኛው አርቲስት አንድ ግለሰብ አይደለም፡፡ እኔ እንደ አንድ ሰው ያየኋቸው ሁለት ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱም በቴሌቪዥን አልፎ አልፎ የምናያቸው ዝነኛው ባለ ከበሮ ሽማግሌ እና ስሟን ለጊዜው መለየት ያቃተን ወጣቷ የከበሮ ተጫዋች ናቸው፡፡ እነዚህን አርቲስቶች ያየሁበት አጋጣሚ ራሱ ለየት ያለ ትዝታ ጥሎብኛል፡፡
      ዘመኑ እንደ ኢትዮጵያው አቆጣጠር በ1980 ነው፡፡ በጊዜው ዝነኛ የነበረው የትግራይ ክፍለ ሀገር የኪነት ቡድን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወረ ዝግጅቱን ሲያቀርብ የኛዋ ገለምሶም በረከቱ ደርሶአት ነበር (በዘመኑ ገለምሶ የሐብሮ አውራጃ ዋና ከተማ ሰለነበረች አዋሽን የተሻገረ ሁሉም ኪነት እኛ ዘንድ ይመጣ ነበር)፡፡ ታዲያ ድሮ በምንሰማው የትግርኛ ዘፈን ውስጥ ከበሮው “ግድፍ! ግድፍ! ግድፍ!” እያለ ማስገምገሙን እንጂ እንዴት ይመታ እንደነበረ ምንም መረጃ አልነበረንም፡፡ የትግራይ ኪነት ወደኛ ሲመጣ ግን ተአምረኛው ሽማግሌና ወጣቷ ተጫዋች የከበሮውን አስደናቂ ትርኢት በዐይናችን እንድናየው አደረጉን፡፡ በዚያች ምሽት ሽማግሌው ወደ ላይ “ዝል..ዝል…” እያሉ  ከበሮውን ይደፍቃሉ፡፡ ወጣቷም እየተሸከረከረችና ሹሩባዋን እያሰናሰለች ከበሮውን ታተረማምሰዋለች፡፡ በተለይ የወጣቷ እንደ እንዝርት መሽከርከር ቢያስደንቀን ብዙዎቻችን ፊልም የምናይ እንጂ እውነት አልመስልህ ብሎን ነበር፡፡
     ዘፋኙ ጨዋታውን ሲያበቃ ህዝቡ “ይደገም… ይደገም.. ይደገም… “ እያለ በጋለ ጭብጨባ ጥያቄውን አቀረበ፡፡ ይሁንና ካባ የለበሰው የመድረኩ መሪ “ክቡራንና ክቡራት ወገኖቼ! ይደገም ያላችሁበት ምክንያት ገብቶኛል፡፡ በከበሮው ትርዒት የተማረካችሁ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ የትግራይ ጨዋታ በአብዛኛው እንዲህ ዓይነት ነው፡፡ እኛም ይዘናቸው በመጣነው ዘፈኖች በሚበዙት ላይ ሁለቱ ተጫዋቾች እየገቡ ከበሮአቸውን ይጫወታሉ፡፡ ስለዚህ የቅድሙን ጨዋታ ከምንደግም ትርኢቱን በሌላ ጨዋታ ላይ ብታዩት ይሻላል” አለንና ጥያቄአችንን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ መለሰልን (የመድረኩ መሪ በዚያች ምሽት ባየነው ድራማ ውስጥ አሉላ አባነጋን ሆኖ ተውኗል)፡፡ በእውነትም እርሱ እንዳለው ሁለቱ አርቲስቶች በየጨዋታዎቹ ጣልቃ እየገቡ ህዝቡን ሲያስደንቁ አምሽተዋል፡፡ ካደግኩኝ በኋላ ያንን የከበሮ ትርዒት በሌሎች አጋጣሚዎች አይቻለሁ፡፡ የያኔው ግን ምን ጊዜም ቢሆን ከአዕምሮዬ አይጠፋም፡፡ የሚገርመኝ ነገር በዚያ ቡድን ውስጥ ታዋቂዋ አርቲስት ሶፊያ አጽብሃ እንደነበረችበት ከአስር ዓመታት በኋላ ማወቄ ነው፡፡ የትግራይ ወዳጆቼ በቁምጣ የምትዘፍነው እርሷ ናት አሉኝ፡፡
   ሶስተኛው ትዝተኛ አርቲስት ብርሃነ ሀይለ ነው፡፡ ብርሃነ በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ “ሸው በሊ ብለነይ” እያለ ሲጫወት “እንዴት የሚያምር ዘፈን ነው” በማለት በተመስጦ ነበር የሰማሁት፡፡ በወቅቱ ዘፈኑ ትግርኛ ይመስለኝ ነበር፡፡ በኋላ ላይ ግን የትግርኛ፣ ቢለን እና ትግረ ቋንቋዎች ቅልቅል መሆኑን ነው የተረዳሁት፡፡ ብርሀነ እንዲህ ነበር ያለው፡፡
ሸው በሊ ብለነይ ብለነይ
ዝለሊ ብለነይ ብለነይ
አሊሊ ብለነይ ብለነይ
አቲ ጓል ከረነይ ብለነይ
ትርጉሙ እንዲህ ይመስለኛል፡፡
ጨፍሪ አንቺ ብለን ሆይ
ዝለሊ አንቺ ብለን
እልል በይ አንቺ ብለን
አንቺ የከረን ልጅ የብለን፡፡
     ቢለን ኤርትራ ውስጥ የሚኖር ብሄረሰብ ነው፡፡ ብርሀነ የቢለን ቆንጆ ወጣትን እያሰበ ነው ይህንን የተጫወተው፡፡ ዜማው የተዜመው በሰሜንና ምዕራብ ኤርትራ በሚኖሩት የትግረ ህዝቦች ምት ነው (የሙዚቃው beat ሬጌ ቢመስልም ከሬጌ ለየት ይላል)፡፡ ብርሃነ ዘፈኑን በዚያ ዘመን ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ቢጫወተውም ለዛሬም ቢሆን ይሰራል፡፡ የኤርትራና የኢትዮጵያ መለያየት መቼም ቢሆን የህዝቦቻችንን ታሪካዊና ባህላዊ ቁርኝት የሚፍቅ አይሆንም፡፡ 
            *****
    የትግራይ ሙዚቃ በጣም ደስ ይላል፡፡ በደንብ ቀርባችሁ ካጣጣማችሁት ልብን በሐሴት ይሞላል፡፡ አርቲስቶቹ ከልቡ ሲያቀናብሩት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከልቡ ይፈነድቅበታል፡፡ እንደምሳሌም ኪሮስ አለማየሁንና በቅርቡ ውጤታማ ለመሆን የበቁትን  አብረሃም ገብረ መድህንን እና ማህሌት ገብረ ገርግስን መጥቀስ ይቻላል፡፡
      
የትግራይ ሙዚቃ እንደ አብዛኛው የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች ሙዚቃ በባለ አምስት ቁልፍ መደብ ላይ የተመሰረተ ( based on pentatonic scale) ነው፡፡ ቅኝቱን በትክክል መግለጽ ይከብደኛል፡፡ ሆኖም በትግራይ ምድር ቢያንስ ሶስት ዓይነት ምቶች እንዳሉ ማንም በቀላሉ አይቶ ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡  አንደኛው ምት ብዙዎቻችን የምናውቀውና “ግድፍ…ግድፍ…” እያለ በሚደለቀው የከበሮ ጉምጉምታ የሚቀናጀው ነው፡፡ ይህ ምት ሁለት ጫፎች እንዳሉት ልብ በሉ፤ ዘፈኑ ሲጀምር ከበሮው “ግድፍ…ግድፍ..” ብቻ ነው የሚለው፤ ወደ ማብቂያው አካባቢ ግን “ግድፍድፍ….ግድፍድፍ….” እያለ በሀይለኛ ድምጸት የሚወርድ ድለቃ ነው የምትሰሙት፤ የእስክስታው ዘውግም ከከበሮው ምት ጋር ይቀየራል፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ዘገም እያለ የሚሄደውና ከብዙ የአማርኛ ምቶች ጋር የሚመሳሰለው ነው፡፡ እንደምሳሌም ኪሮስ አለማየሁ “አወይ ላሌ ላሌ… ላሌዋ” እያለ የዘፈነበትን ዜማ መጥቀስ ይቻላል (የዚህ ምት መነሻው የተምቤን አውራጃ ነው ሲባል የሰማሁ ይመስለኛል)፡፡ ሶስተኛው በራያ አዘቦና በአንዳንድ የእንደርታ አካባቢዎች የሚዘወተረው የ“ላሌ ጉማ..” ምት ነው፡፡ ይህኛው ምት ከሌሎቹ ፈጠን ይላል፡፡ በትግራይ ምድር እነዚህ ሶስት ምቶች መኖራቸው የተረጋገጠ ነው፡፡ ሌሎች ምቶች መኖራቸውን ብጠረጥርም እርግጠኛ ስላልሆንኩ ነው ያልጻፍኳቸው፡፡
             *****
   ከላይ እንደገለጽነው ትግራይ በጉብኝት ሊስታችን ውስጥ አለች፡፡ በመሆኑም ሁኔታዎች ሲመቻቹ ያንን ተናፋቂ መሬት ማየታችን አይቀርም (ሰፖንሰር ከተገኘ ግን ዛሬም ጎብኝተነው እዚያ ያለውን በረከት ልንጽፍላችሁ እንችላለን….… ግብዣ ተገኝቶ ነው እንዴ? ሆሆይይ!!)፡፡ እናንተም ምኞቴ እንዲሳካልኝ “ዱዓ” አድርጉልኝ እስቲ (ይሄ ምኞት የሚሉት ነገር እንዳይገድለኝ ብቻ)፡፡ 
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ታሕሳስ 19/2006



ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——–
    ኦሮማይ ከልቡ መጽሐፍ ነው፡፡ በአማርኛ ልብ-ወለድ መጻሕፍት (Novel) ታሪክ በጣም አነጋጋሪውና አከራካሪው መጽሐፍ ነው፡፡ እስከ አሁን ድረስ የህዝብ ፍቅር ካልተነፈጋቸው ጥቂት መጻሕፍት አንዱም ነው፡፡ በህይወቴ ብዙ ጊዜ እየደጋገምኩ ካነበብኳቸው መጻሕፍት መካከልም በመጀመሪያው ረድፍ ይሰለፋል፡፡ ይሁንና ሰዎች ለዚህ መጽሐፍ ያላቸው አድናቆት እንደየ አመለካከታቸው ይለያያል፡፡
  መጽሐፉ የብዙዎቹን አትኩሮት የሳበው ታሪኩ እውነት ነው ስለተባለ እና በመጽሐፉ ሳቢያም የደራሲው ህይወት ለአደጋ በመጋለጡ ይመስለኛል፡፡ ከመጽሐፉ ዐቢይ ገጸ-ባህሪያት አንዱ የሆኑት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ “የደም እምባ” በተሰኘው መጽሐፋቸው ተመሳሳይ እይታ አንጸባርቀዋል፤ እንደ ሻለቃ ዳዊት አባባል ኦሮማይ ባይታገድ ኖሮ ተወዳጅነቱ ይሄን ያህል አይገዝፍም ነበር፡፡ ሆኖም እኔ በዚህ አባባል አልስማማም፡፡ ደራሲው ባይሞት እና ታሪኩ እውነተኛ ባይሆን እንኳ “ኦሮማይ” ተደናቂ የመሆንን እድል አያጣም ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ ለዚህም በርካታ አብነቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡
  
   “ኦሮማይ” በቅድሚያ ቀልብን የሚስበው በአጻጻፍ ብሂሉ ነው፡፡ ደራሲው ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው አጫጭር ዐረፍተ ነገሮችን ይጠቀማል፡፡ ይህም አንባቢው የመጽሐፉን የትረካ ቅደም ተከተል ሳይስት ድርሰቱን ያለድካም እንዲያጣጥም ያግዘዋል፡፡ ደራሲው ጠጣር ሃሳቦችን በቀላሉ ይዘረዝራል፡፡ የዘመኑ መንግሥት አሰራርን ለተደራሲው በሚገባው ቋንቋ ቀለል አድርጎ ያስረዳዋል፡፡ በሌላ በኩል መጽሐፉ ኪናዊ ውበቱን እንዳይስት ደራሲው በእጅጉ ተጠቧል፡፡ ዘይቤአዊ አባባሎችን ከዘመኑ የአነጋገር ፋሽን ጋር እየቀላቀለ አንባቢውን ያዝናናዋል፡፡ በተለይም “ኦሮማይ” ፈጠራ እየነጠፈ በዘመቻ ግርግር እና በንድፈ-ሓሳብ ዝብዘባ የሚፈበረኩ ቃላት የድርሰቱን ጎራ እያጠለሹ በመጡበት ዘመን አንባቢው በማይሰለቸው የቋንቋ ጥበብ የተጻፈ በመሆኑ የደራሲውን ልዩ ተሰጥኦ በጉልህ ያስረዳል፡፡ ሆኖም ኦሮማይ የዚያ ዘመን ድርሰት ብቻ አይደለም፡፡ በዚህ ዘመንም እንኳ ተደግመው ሊጻፉ ከማይችሉ ድርሰቶች መካከል ሊመደብ ይችላል፡፡ 
      ይበልጥ አስደናቂው ነገር ደግሞ ወዲህ ነው፡፡ ደራሲው ያንን ውብ መጽሐፍ የጻፈው በጥቂት ወራት ውስጥ ነው፡፡ ይገርማል! ሰውዬው በወቅቱ ምክትል የማስታወቂያ ሚኒስትር ነበር (በደንበኛ ስሙ የማስታወቂያ ሚኒስቴር ቋሚ ተጠሪ ይባል ነበረ)፡፡ የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ሆኖም ይሰራ ነበር፡፡ በአዲስ ዘመን እና በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጦች ዝግጅትም ይሳተፋል፤ ዝግጅታቸውን በበላይነት ይቆጣጠራል፡፡ ቱባ ባለስልጣን በመሆኑ የብዙ ኮሚቴዎች አባል መሆኑም ይታመናል፡፡ በርካታ የቢሮክራሲ ስራዎችም ነበሩት፡፡ እና ከነዚህ ሁሉ የስራ ጋጋታዎች ጋር የሚታገል ሰው ያንን የመሰለ ውብ መጽሐፍ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ እንዴት ብሎ ነው የጻፈው? ይህንን በቀላሉ ማመን ይቻላል? በትርፍ ጊዜው መጻፉ ይቅርና የሙሉ ጊዜ ደራሲ ቢሆን እንኳ አስቸጋሪ መሆኑ አይቀርለትም፡፡ ሰውዬው ግን በዓሉ ነውና ቻለው! የስራ መደራረብ “ሳይበግረው” ኦሮማይን ከዘጠኝ ወራት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ እንዲያ ከሽኖ አቀረበው (የቀይ ኮከብ ዘመቻ ያበቃው በየካቲት ወር 1974 ነው፤ ኦሮማይ የታተመው በታህሳስ ወር 1975 ነው)፡፡ ችሎታ ማለት እንዲህ ነው!!
 ለኦሮማይ ዘመን አይሽሬነት ሁለተኛ አብነት ሆኖ የሚጠቀሰው ደግሞ የመጽሐፉ ጭብጥ ነው፡፡ በዚህ ላይ በርካታ ሰዎች የተለያየ አስተያየት ነው ያላቸው፡፡ አንዳንዶች በዓሉ ኦሮማይን የጻፈው የቀይ ኮከብ ዘመቻ ውጥረትና ውድቀትን ለመግለጽ ስለፈለገ ነው ይላሉ፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ “የመጽሐፉ ጭብጥ በርዕሱና በመጨረሻው ዐረፍተ ነገር ላይ ነው የሚገኘው” ብለው ነገር፡፡ አቶ መለስ ንግግራቸውን ሲያሰፉም “በዓሉ በመጽሐፉ  “እናንተ ደርጎች በኤርትራ ላይ ሙዝዝ ካላችሁ በአዲስ አበባ ያላችሁንም ስልጣን ታጣላችሁ” የሚል መልዕክት ነው ያስተላለፈው” ብለዋል፡፡ አቶ መለስ ይህንን ትንተና የሰጡት ኢትዮጵያ ከኤርትራ ጋር የአልጀርሱን ስምምነት ፈርማ የድንበር ኮሚሽኑን ውሳኔ በምትጠባበቅበት ወቅት “የስምምነቱ አካሄድ ኢትዮጵያን የሚጎዳ ነው” የሚል ሃሳብ ለሰነዘሩ ተቃዋሚዎች መልስ በሚሰጡበት ጊዜ ነው (ባልሳሳት ጊዜው የካቲት 1994 ይመስለኛል)፡፡ ሆኖም የኦሮማይ ጭብጥ በእንዲህ ዓይነቱ የፖለቲካ ዘውግ ብቻ የታጠረ አይደለም፡፡ ኦሮማይ በዘመኑ “አይነኬ” (taboo) የነበሩ በርካታ ጉዳዮችን ይነካካል፡፡ ለማስረዳት ይፈቀድልኝ፡፡
   
   የደርግ መንግሥት በወቅቱ የሀገሪቱን ህዝብ ከአቅሙ በላይ እያሯሯጠው ነበር፡፡ ህዝቡ በየዓመቱ ከሚመጣበት የዘመቻ መአት ሳያገግም በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶም ተሰምቶም የማያውቀው ግዙፉ የቀይ ኮከብ ሁለገብ ዘመቻ በጫንቃው ላይ ወረደ (ዘመቻው የጠየቀው የሰው ሀይልና ማቴሪያል ሳይደመር ሁለት ቢሊዮን ብር ወጥቶበታል፤ ይህም በወቅቱ ከሀገሪቷ በጀት ግማሽ ያህሉን ይሸፍናል)፡፡ ሆኖም በዘመኑ ወታደራዊው መንግሥት ያሻውን ቢያቅድና ቢፈጽም አይደፈሬ ነውና ማንም ሰው አፍ አውጥቶ አልተቃወመውም፡፡ በዓሉ ግርማ ግን ለመጪውም ዘመን ትምህርት በሚሆን መልኩ የቀይ ኮከብ ዘመቻን በግልጽ ቋንቋ ሄሶታል፡፡ ለምሳሌ በመጽሐፉ ውስጥ የጋዜጠኛ ጸጋዬ ኃይለማሪያም እጮኛ እንዲህ ትላለች፡፡
  
  “ኤጭ እቴ! ለሁሉም ነገር ቸኩሎ መሞት! ነጋ ጠባ ዘመቻ! እድገት በህብረት ብሎ ዘመቻ! ለጦርነት ዘመቻ፡፡ የኢኮኖሚ ግንባታ ዘመቻ፡፡ ማይምነትን ለማጥፋት ዘመቻ፡፡ የቁጥጥር ዘመቻ፡፡ አሁን ደግሞ የኤርትራን ችግር ለመፍታት ዘመቻ፡፡ የዘመቻ ባህል ፈጥረናል፡፡ ያለዘመቻ ኖረን የምንሞትበት ቀን መቼ ይሆን?”  (ኦሮማይ ፤ ገጽ 9)
 ጋዜጠኛው የመንግሥት ባለስልጣን ሆኖ ለእጮኛው ንግግር የሰጠው ምላሽ ይበልጥ የሚደንቅ ነው፡፡ “ጊዜ ያጥረናል፤ እብዶች ነን፤ ችኩል ትውልድ፤ ያበደ ትውልድ…” ወዘተ.. ይላታል (ኦሮማይ፤ ገጽ 10)
  በአንድ በኩል ጸሓፊው የዘመኑ ባለስልጣናት ለቀይ ኮከብ ዘመቻ መሳካት አኩሪ ገድል ሲፈጽሙ ያሳየናል፡፡ ወዲያው ዞር ይልና ደግሞ የመንግሥቱ የቀን ቅዠትና ሀገር አጥፊ ፖሊሲ ያስከተለውን ቀውስ በራሳቸው በባለስልጣናቱ አንደበት ይገልጽልናል፡፡ ለምሳሌ ከመጽሐፉ ዐቢይ ገጸ-ባህሪያት አንዱ የሆነው ኢኮኖሚስቱ መጽሐፈ ዳንኤል ዘመቻው በሀገሪቱ ምጣኔ ሀብት ላይ የሚፈጥረውን አሉታዊ ጫና በማስረዳት የዘመኑን አመራር እንዲህ ይሸረድደዋል፡፡
   “ይህንን የቆየ ችግር በዘመቻ እንፈታለን ብለን ስንረባረብ ከአሁኑ ሌላ ችግር እየፈጠርን ነው፤ 450 ከባድ የጭነት መኪናዎች፤ 250 ሼልቶ፣ 200 ከነተሳቢያቸው ወደ ሰሜን ማዞር ምን ማለት ነው? ባጭሩ ኢኮኖሚው ተናግቷል ማለት ነው፤ ደሞ አሁን የመኸር ጊዜ መሆኑን አትርሳ” (ኦሮማይ፤ ገጽ 75)
     ጋዜጠኛው በዚህ አባባል ተናዶ “ስብሰባው ላይ ምን ዘጋህ? ቅድም እንዲህ ብለህ አትናገርም ነበር፡፡ መድረኩ ለማንም ክፍት ነበር፡፡ማን ከለከለህ?” ሲለው መጽሐፈ ዳንኤል “ትቀልዳለህ ልበል?” በማለት በአጭሩ መልሶለታል፡፡ መጽሐፈ ልክ ነው፡፡ አንድ ሰው በሚፈልገው መንገድ ብቻ መደስኮር በሚፈቀድበት ስብሰባ ሐቁን እናገራለሁ ቢል የሚደርስበትን ቅጣት በደንብ ያውቀዋል፡፡ ለዚህም ነው በስብሰባና በጉባኤ ፊት እያስመሰሉ መለፍለፍ እና ለክፉ አሳልፎ የማይሰጥ ወዳጅ ሲገኝ ሐቁን መናገር የዘመኑ ወግ ሆኖ የቆየው፡፡
 
   በተመሳሳይ መልኩ ሰለሞን በትረ-ጊዮርጊስ የተባለው ገጸ-ባህሪ የያኔውን የፕሮፓጋንዳ አካሄድ እስኪበቃው ድረስ ሲወርፍ ይታያል፡፡ “እናንተ ጋዜጠኞች ጭንቀታችሁ ሁሉ ስታቲስቲክስ ነው፤ ይህን ያህል ሄክታር መሬት ታረሰ፤ ይህንን ያህል ህዝብ ተደራጀ፤ ይህን ያህል ሰዎች ከመሀይምነት ተላቀቁ፤ ነው የምትሉት፡፡ እንዲያው ወሬአችሁ ሁሉ ስታቲክቲክስ ነው፤ ዘገባችሁ ሰው ሰው አይሸትም፤ ስለ አሐዝ ስትጨነቁ ሰው ትረሳላችሁ” ይላል (ኦሮማይ፤ ገጽ 67)፡፡ እነኝህን የመሳሰሉ የስርዓቱን ጉድፍ የሚያሳዩ በርካታ አንቀጾችን መልቀም ይቻላል፡፡
    የቀይ ኮከብ ዘመቻ የመጨረሻ ግብ ናቅፋ የሚገኘውን የሻዕቢያ ዋና የዕዝ ማዕከል መቆጣጠር ተደርጎ ይታሰብ ነበር፡፡ ሆኖም ናቅፋ በቀላሉ የምትደፈር ሆና አልተገኘችም፡፡ ሺዎች እንደ ቅጠል ረግፈዋል፡፡ ሺዎች ቁስለኛና ምርኮኛ ሆነዋል፡፡ ሁኔታውን በቅርበት የታዘበው ጋዜጠኛ ጸጋዬ ኃይለማሪያም ጦርነቱ ከኪሳራ ውጪ የሚፈይደው ነገር እንደሌለ ተገንዝቧል፡፡ ከናቅፋ ወደ አፍአበት ሲመለስ “አይዞን! ገና ሺህ ናቅፋዎች ይጠብቁናል” ብሎ ለተናገረው የዘመኑ ከፍተኛ ባለስልጣን “እኔ አንድ ናቅፋ ከወዲሁ በቅቶኛል፤ የጦርነትን አስከፊ ገጽታ ከአሁን በኋላ ላለማየት ቆርጫለሁ” በማለት ተቃውሞውን ገልጿል (በዓሉ ጦርነቱን ከተቃወመባቸው ዐረፍተ ነገሮች መካከል ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠው ይህኛው ነው)፡፡
       *****
 “ኦሮማይ” ፈርጀ ብዙ የዕውቀት ድርሳን ነው፡፡ ረጅምና ውስብስብ የሆኑ እውነተኛ ታሪኮችን እጥር ምጥን አድርጎ በቀላሉ ያስነብበናል፡፡ ለምሳሌ የኤርትራ ችግር መሰረታዊ ምንጭ ምን እንደሆነ መረዳት የሚፈልግ ሰው ከሰለሞን በትረጊዮርጊስ ታሪካዊ ትንተና ብዙ ቁምነገሮችን ይጨብጣል (ኦሮማይ፡ ገጽ 78-86)፡፡ እንግሊዝ በኤርትራ ምድር የቀበረችው ፈንጂ፤ የኤርትራ ክፍለ ሀገርን ከኢትዮጵያ ጋር ለመቀላቀል የተደረገው ጥረት፤ የጀብሃና ሻዕቢያ አነሳስና በመካከላቸው የተፈጠረው ፍጭት፣ አብዮታዊ ሰራዊት ኤርትራን ከአማጺያን ለማጽዳት ያደረገው ዘመቻ ወዘተ… በሰለሞን አንደበት በሰፊው ተተንትነዋል (እርግጥ ትንተናው ሙሉ በሙሉ ትክክል ነው ለማለት አይቻልም፤ ግማሽ ያህሉ የደርግ መንግሥት በሚፈልገው መልክ የተቀናበረ ነው)፡፡
  
   የጎሪላ እና መደበኛ የውጊያ ስልትን በተነጻጻሪ ማወቅ የሚፈልግ ሰው ከኦሮማዩ ኮሎኔል ታሪኩ ወልዳይ ትንታኔ ብዙ ነገሮችን ይማራል፡፡ ኮሎኔል በትሩ ተሰማ እና አጋዥ ቡድኑ (እነ ተክላይ ዘድንግል ያሉበት) የዘመኑ የኢንተሊጀንስ ጥበብና ስልት ምን ይመስል እንደነበር በቃልና በድርጊት ያሳዩናል፡፡ ጋዜጠኛው ጸጋዬ ኃይለማሪያም አስቸጋሪውን የናቅፋ ተራሮች የመሬት አቀማመጥ ለዓይናችን ወለል ብሎ እስኪታየን ድረስ በማይሰለቸው ብዕሩ እያጣፈጠ ይተርክልናል፡፡ ስዕላይ ባራኺ እና ጓዶቹ ደግሞ የሚያስገርሙ ጀብዶችን እየተገበሩ ሻዕቢያ በሰርጎ ገቦቹ አማካኝነት አስመራን እንዴት ያሸብራት እንደነበር ያሳዩናል፡፡ የአስመራ ነዋሪዎች የአኗኗር ወግና ማሕበራዊ ህይወት፣ የከተማዋ ታዋቂ ሰፈሮችና ሆቴሎች፤ የመንገዶቹ ውበትና አቀማመጥ ወዘተ… በመጽሐፉ ዘርዘር ብለው ተጽፈዋል፡፡ በኔ እይታ አንድ ሰው ልብ ወለድ ተብሎ የተጻፈውን “ኦሮማይ”ን ቢያነብ ከአስር መጻሕፍት የሚያገኘውን ዕውቀት ሊገበይ ይችላል፡፡
        *****
     እንደዚያም ሆኖ ግን “ኦሮማይ” ሙሉ በሙሉ እውነተኛ ታሪክ አይደለም፡፡ ደራሲው የመጽሐፉን ተነባቢነት ለማጉላት ምናባዊ ገጸ-ባህሪዎችንና ታሪኮችን ጨማምሯል፡፡ ለምሳሌ ደራሲው የሁለት ሰዎችን ታሪክ አዳብሎ “ስዕላይ በራኺ” የተባለ ገጸ-ባህሪ ፈጥሮልናል፡፡ እንደዚሁ ደግሞ በመጽሐፉ ውስጥ የሻዕቢያ ሰዎች በዚሁ ስዕላይ በራኺ በተባለ ገጸ-ባህሪ መሪነት የሚያካሄዱት “ኦሮማይ” የተሰኘ ስውር ኦፕሬሽን የደራሲው ፈጠራ ነው (“ቢሮክራሲ” የተባለው የስለላ ኔትወርክ ግን ትክክለኛ ነው)፡፡
 
   ከኦሮማይ ገጸ-ባህሪያት መካከል ኮሎኔል መንግሥቱ ሀይለማሪያምና ኢሳያስ አፈወርቂን የመሳሰሉት በእውነተኛ ስማቸው ተጠቅሰዋል፡፡ አንዳንዶቹ ግን ስም የለሽ ሆነው በድርጊታቸው ብቻ ተገልጸዋል (ለምሳሌ “የቀይ ኮከብ ሁለገብ ዘመቻ ዋና ጸሐፊ” ተብለው በስራ መደባቸው ብቻ የተጠቀሱት ባለስልጣን አቶ አማኑኤል አምደሚካኤል ናቸው)፡፡ ከፊሎቹ ገጸ-ባህሪያት በእውነታው ዓለም የሚታወቁበት ስም በመጽሐፉ ውስጥ ተቀይሯል፡፡ ከነርሱ መካከል የጥቂቶቹ ትክክለኛ ስም እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
1.      ኮሎኔል በትሩ ተሰማ= ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደ ሥላሴ (በደርግ መንግሥት የህዝብ ደህንነት ጥበቃ ሚኒስትር፤ ሆኖም ኮሎኔሉ “የኔ ምክትል ነው እንጂ እኔ አይደለሁም፤ እኔ በቀይ ኮከብ ዘመቻ አስመራ አልሄድኩም” በማለት አስተባብሏል)።
2.     ኮሎኔል ታሪኩ ወልዳይ= ኮሎኔል ተሻገር ይማም (የአንበሳው ሶስተኛ ክፍለ ጦር ዋና አዛዥ የነበረ፤ በ1974 በናቅፋ በተካሄደው አደገኛ ጦርነት ማብቂያ ላይ ራሱን የገደለ)።
3.     መጽሐፈ ዳንኤል= አቶ ፋሲካ ሲደልል (የኢሠፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የማዕከላዊ ፕላን ሚኒስትር የነበረ)
4.     የሺጥላ ማስረሻ= አቶ ሽመልስ ማዘንጊያ (የኢሠፓ የፖሊት ቢሮ አባልና የርዕዮተ ዓለም ጉዳዮች ሃላፊ የነበረ)
5.     ጸጋዬ ሀይለማሪያም= የበዓሉ ግርማ ግርማ እና የቴሌቪዥን ጋዜጠኛው የጌታቸው ኃይለማሪያም ቅልቅል ይመስላል፡፡  
6.     ተድላ ረጋሳ= ሻለቃ ፍሰሓ ገዳ (የኢሠፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የደርግ መንግሥት የፕሮቶኮል ሹም)
7.     ሰለሞን በትረ ጊዮርጊስ= ሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ (በቀይ ኮከብ ዘመን የኤርትራ ክፍለ ሀገር ኢሠፓአኮ ተጠሪ እና የክፍለ ሀገሩ የበላይ አስተዳዳሪ፣ በኋላም የእርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን ኮሚሽነር፤ በ1978 ከደርግ መንግሥት ተነጥሎ ወደ ውጪ ሀገር የኮበለለ)
8.     ስዕላይ ባራኺ= የሁለት ሰዎችን ታሪክ በመቀላቀል የተፈጠረ ነው፡፡ አንደኛው ተስፋሚካኤል ጆርጆ ነው (አቶ ተስፋሚካኤል በሀይለስላሴ ዘመን የደቀምሐረ ወረዳ ገዥ የነበረ ሲሆን በ1963 ኢሳያስ አፈወርቂን ከሲ.አይ.ኤ ጋር በማገናኘት ቁልፍ ሚና ተጫውቷል፣ ይህ ሰው በ1984 መጨረሻ ላይ በሻዕቢያ አዳኝ ኮማንዶዎች አዲስ አበባ ውስጥ ቫቲካን በሚባለው ሰፈር ተገድሏል)። ሁለተኛው ሰው ተክላይ አደን ይባላል (ተክላይ አደን የሻዕቢያ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የድርጅቱ የፖለቲካ ትምህርት ቤት ሃላፊ ነበር፤ በኋላ እጁን ሰጥቶ በሀገር ውስጥ ሲኖር ከቆየ በኋላ ደርግ ሲደመሰስ ወደ አውሮጳ ሄዷል)፡፡
9.     “ቢሮክራሲ”= አፈወርቂ ተወልደ መድሕን (ደሴ የተማረ የሻዕቢያ የውስጥ አርበኛና ሰላይ፣ “ቢሮክራሲ” በሚል ስም የሚታወቀውን የስለላ ኔትወርክ የሚመራው እርሱ ነው፡፡ በኋላ ግን ድሬ ዳዋ ላይ ተይዞ ተረሽኗል)፡፡
       *****
ስለኦሮማይ ይህንን ብያለሁ፡፡ ወደፊት አዲስ ነገር ከተገኘ መመለሴ አይቀርም፡፡ እስከዚያው ሌሎቻችሁ የምታውቁትን ጨምሩበት፡፡
   ሰላም!
አፈንዲ ሙተቂ
ሸገር-አዲስ አበባ
ጥቅምት 13/2006


—–
ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——
ከሰው ቤት ትቼው የሄድኩትን የመጽሐፍ መደርደሪያዬን ስበረብር “መስታወት” የተሰኘ የድሮ መጽሔት ምዝዝ ብሎ ወጣ፡፡ እንደ ዋዛ ዐይኔን ከመፅሔቱ ሽፈን ላይ ጣል ሳደርግም የ“አያልነሽ” ፎቶ ታየኝ፡፡ ከፎቶው አጠገብም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ሰፍሮ አነበብኩኝ፡፡
   “አቶ መለስ የራሷ ድርጅት የላትም፤ እራሷ ድርጅት ትሆን እንጂ” ያሉት ሳያውቁ ቀርተው ነው ብሎ ማመን ያዳግተኛል”፡፡
    አቶ መለስ ዜናዊ እንዲህ ማለታቸው የተነገረው ገና ጫካ ሳሉ ከሲ.አይ.ኤው ፖል ሂንዝ ጋር ባደረጉት ውይይት እንደሆነ ተዘግቧል (በርግጥ አቶ መለስ ያሉት “ራሷ ድርጅት ናት” ሳይሆን “እርሷ በራሷ የምትታገል ታጋይ ናት እንጂ ከየትኛውም ድርጅት ጋር የወገነች አይመስለኝም” ነው፡፡ ፖል ሄንዝ የውይይቱን ጭማቂ በአሜሪካ ይፋ ካደረገ በኋላ በተለያዩ መጽሔቶች ላይ ታትሞ ነበር)፡፡
   ወይ “አያልነሽ”! ስንቱን ያንቀጠቀጠች ጀግና መሰለቻችሁ?! ለደርግ ራስ ምታት ሆና በጎንደር እና በጎጃም እንደፈለገችው ትንሸራሸር ነበር፡፡ በርሷ ጀግንነት የተመሰጠው የጎጃም ህዝብ “አያልነሽ!….ክላሽ ልግዛልሽ!” እያለ በሰርግ ላይ የሚዘፈን የአጀብ ዜማ እስከ መውጣት ደርሷል፡፡ በደርግ እግር የተተካው ኢህአዴግም በርሷ ምክንያት ክፉኛ ታውኮ ነበር፡፡ እርሷ ስትያዝ ደግሞ ኢህአዴጎች በየስፍራው የደስታ መድፍ መተኮሳቸው በሰፊው ተወርቷል፡፡ 
   የ“አያልነሽ” ነገር በጊዜ ሰረገላ ወደ ኋላ እያበረረኝ የድሮ ትዝታዬን ቀሰቀሰው፡፡ ስለ“አያልነሽ” አመጸኛነት ሳስብ የያኔው ትውልድ የዓላማ ጽናት ከፊቴ እየመጣ በሃሳብ አስተከዘኝ፡፡ “የኔ ትውልድስ እንደዚያ ዓይነት ፋኖዎችን ያወጣ ይሆን?” እያልኩ ደጋግሜ ራሴን ጠየቅኩኝ፡፡
  
    ከሀገር ጭምር አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ መነጋገሪያ ለመሆን የበቃችው ያቺ ሴት ዛሬ በትግሉ ውስጥ የለችም፡፡ ወደ ሰላማዊ ኑሮ ገብታ የልጆች እናት ሆናለች፡፡ ሆኖም የታሪካችን አካል ነችና በወቅቱ ስለርሷ ላልሰሙት ታሪኳን የማድረስ ግዴታ አለብን፡፡ እነሆ የአያልነሽን ወግ ከብዙ በጥቂቱ ልናወጋችሁ ነው፡፡   
*****
   የደርግ መንግሥት በግንቦት 20/1983 ሲገረሰስ ኢሕአዴግ ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመጣመር የሽግግር መንግሥት እንዲመሰርት ተወስኖ ነበር፡፡ ኢሕአዴግም በለንደኑ ኮንፈረንስ የተወሰነውን ውሳኔ ተቀብሎ ለተግባራዊነቱ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ ለልዩ ልዩ ድርጅቶችም የጉባኤ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ በዚህም መሰረት በርካታ ድርጅቶች ወደ አዲስ አበባ መጉረፍ ጀመረ፡፡ ይሁንና በዚያ ዘመን ከኢህአዴግና ከኦነግ ቀጥሎ ከፍተኛ ስም የነበረው የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ሀይሎች ቅንጅት (ኢ.ዲ.ሀ.ቅ) በጉባኤው እንዳይሳተፍ ተከለከለ (ኢዲሀቅ የኢህአፓ፣ የመኢሶን፣ የኢፒዲኤ እና የኢዲዩ ጥምረት ነበር)፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያ ጊዜያዊ መንግሥት ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ኢዴሀቅ በጉባኤው ላይ እንዳይሳተፍ የተከለከለበትን ምክንያት በሰኔ ወር አጋማሽ ለጋዜጠኞች ሲያብራሩ
  “ኢዴሀቅ በጊዜያዊ መንግሥቱ ላይ ጦርነት አውጇል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ያወጀውን የጦርነት አዋጅ አላነሳም፤ ይህም የጦርነት አዋጅ ድርጅቱ በሰላምና በዲሞክራሲ ጉዳይ ላይ በሚመክር በዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት እንደሌለው ያሳያል” ብለው ነበር፡፡
  
  አቶ መለስ እንዲህ በማለት የገለጹት ኢዴሀቅ የተመሰረተው በመጋቢት 1983 ነበር፡፡ ይሁንና ይህ ድርጅት በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ በጊዜያዊ መንግሥቱ ላይ ጦርነት አውጇል መባሉ ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆኖ ነበር (ጊዜያዊ መንግሥቱ በግንቦት ወር 1983 የደርግ ውድቀትን ተከትሎ ነበር የተመሰረተው)፡፡ ኢዴሀቅ የደርግ ብሔራዊ ሸንጎ በመጨረሻ ጉባኤው ያስተላለፈውን ውሳኔ በመደገፍ ሚያዚያ 16/1983 መግለጫ አውጥቶ ነበር፡፡ በመሆኑም አቶ መለስ “ኢዴሀቅ ጦርነት አውጇል” ያሉት ያንን መግለጫ ተንተርሰው እንደሆነ በርካታ የፖለቲካ ተንታኞች በወቅቱ የተናገሩት ጉዳይ ነው፡፡
           *****
   ከጥቂት ጊዜ በኋላ አቶ መለስ የተናገሩት የጦርነት ወሬ ውሸት እንዳልሆነ የሚያረጋግጥ ጭምጭምታ ተሰማ፡፡ ከወደ ጎንደርና ጎጃም አካባቢ የጦርነት ዜና መናፈስ ጀመረ፡፡ ኢህአዴግ እና አንድ ያልታወቀ ሀይል ብርቱ ውጊያ ላይ መሆናቸው ተነገረ፡፡ የዚያ ያልታወቀ ሀይል ኮማንደርም ሴት ናት መባሉ ደግሞ የብዙዎችን ቀልብ ሳበ፡፡ ያ ሀይል ማን ነው? ሴቲቷስ ማን ናት?
   ኢህአዴግ በወቅቱ ስለውጊያው ትንፍሽ አላለም፡፡ ከአሜሪካና ከአውሮፓ የሚተላለፉ የተቃዋሚ ሬድዮዎችና አንዳንድ በራሪ ወረቀቶች ነበሩ ዜናውን ሲያስተላልፉ የነበሩት፤ የአሜሪካ ድምጽ ሬድዮም ወሬውን አልፎ አልፎ ይነካካ ነበር፡፡ ከነዚያ ምንጮች ለማወቅ እንደተቻለው በወቅቱ ከኢህአዴግ ጋር ሲዋጋ የነበረው የኢህአፓ ሰራዊት ነው፡፡ የሰራዊቱ ኮማንደርም “አያልነሽ” ነበረች፡፡ በርሷ የሚመራው ጦር ከ1970ዎቹ አጋማሽ ጀምሮ በምዕራብ ጎንደር ቆላማ ክፍል (ወገራ፣ ጭልጋ፣ ቋራ ወዘተ…) እና በመተከል አውራጃ ሲንቀሳቀስ ነበር፡፡ (“መተከል” በዘመኑ የጎጃም ክፍለ ሀገር ትልቁ አውራጃ ሲሆን በደርግ የመጨረሻ ዓመታት ራሱን ችሎ “የመተከል አስተዳደር አካባቢ” ተብሎ ተሰይሞ ነበር፡፡ “መተከል” በአሁኑ ዘመን የቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል አካል ሆኗል)፡፡
 
    አያልነሽ ደርግን ስትዋጋ ለብዙዎች ተራ ሽፍታ ትመስል ነበር፡፡ ይህም የደርግ ፕሮፓጋንዳ ክፍል የኢህአፓን መኖር ለህዝቡ ለማሳወቅ ባለመፈለጉ ምክንያት የመጣ ነው፡፡ ደርግ “ኢህአፓ ተደምስሷል” ብሎ በይፋ አውጆ ስለነበር አያልነሽ የኢህአፓ ኮማንደር መሆኗ ከተገለጸ “ኢህአፓ” አሁንም አለ እንዴ?” የሚል ጥያቄ ከህዝቡ ይነሳብኛል የሚል ፍርሃት ነበረው፡፡ ለዚህም ነበር የደርግ ሰዎች ኢህአፓን ትተው “ አያልነሽ… አያልነሽ..” ሲሉ የነበሩት፡፡ እንደ ደርግ ሰዎች አባባል “አያልነሽ ቀኛዝማች ስሜነህ የሚባሉ ጎንደሬ ልጅ ናት፡፡ የምትዋጋውም አባቷ በአብዮት ሀይሎች ስለተገደለባት የአባቷን ደም ለመበቀል” ነው፡፡
   ነገሩ ግን እውነት አልነበረም፡፡ አያልነሽ የኢህአፓ ሰራዊት የምዕራብ ክፍል ኮማንደር ነበረች፡፡ ከሰራዊቱ ጋር የተቀላቀለችውም በቂም በቀል ተነሳስታ ሳይሆን ድርጅቱ የከተማ የትጥቅ ትግሉን ትቶ ወደ ገጠር ባፈገፈገበት ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ አያልነሽ የኢህአፓ አባል የሆነችው በልጅነቷ (በአስራ አንድ ዓመቷ) ነው፡፡ ይህች ሴት የተወለደችው በጎንደር ከተማ ሲሆን እውነተኛ ስሟ “የዓለም ገዥ ከበደ” ነው፡፡ “አያልነሽ” በኢህአፓ አባልነቷ የተሰጣት የትግል ስሟ ነው፡፡ እስከ አሁን ድረስ የምትታወሰውም በዚህ ስም ነው፡፡
           *****
   አያልነሽ በዘመነ ደርግ ሰራዊቷን በቆራጥነት መምራት ቀጠለች፡፡ በተለይ ጎጃምና ጎንደር የራሷ ነጻ ግዛት እስኪመስል ድረስ በህዝቡ ዘንድ ስሟ ተደጋግሞ ይወሳ ነበር፡፡ በ1980 መጨረሻ ገደማ በእርዳታ ሰራተኛነት ሽፋን የመተከል አውራጃ ዋና ከተማ የነበረችውን ፓዌን የጎበኘው የሲ.አይ.ኤው ዝነኛ ሰላይ ፖል ሄንዝ የአካባቢው ሰው ለአያልነሽ የነበረውን አድናቆት ልብ ብሎ አስተዋለ፡፡ እናም ከዓመት በኋላ ወደ ሰሜን አሜሪካ ለጉብኝት የጋበዘውን ወጣቱን የህወሐትና የኢህአዴግ መሪ አቶ መለስ ዜናዊን ስለአያልነሽ ጠየቀው፡፡ ታዲያ አቶ መለስም ልክ እንደ ደርግ ሰዎች የኢህአፓን ስም ላለማንሳት ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ ነበረበት፡፡ በወቅቱ የኢህዴን (የአሁኑ ብአዴን) ስም እንጂ የኢህአፓ ስም ተጋንኖ እንዲወራ አይፈለግም ነበርና “አያልነሽ በራሷ የምትታገል ታጋይ ናት እንጂ በድርጅት የታቀፈች አይመስለኝም” በማለት ጉዳዩን በደንብ ሳያወሳው አለፈው፡፡
  
   ደርግ ተደመሰሰ፡፡ ኢህአዴግም በርሱ ቦታ መንግሥት ሆነ፡፡ የአያልነሽ ቀጣይ ትግልም ከአዲሱ መንግሥት ጋር ሆነ፡፡ ሁለቱ ሀይሎች ከአሲምባ ጀምሮ ይተዋወቃሉ፡፡ ሁለቱም ከፍተኛ ግጭቶችን አድርገዋል፡፡ ይሁንና ኢህአዴግ በጎንደርና በጎጃም የነበረው የኢህአፓ ሰራዊት በገበሬው ልብ የገባ ሰላልመሰለው አያልነሽና ጦሯን በቀላሉ የሚያባርራቸው ፋኖዎች አድርጎ ነበር የገመተው፡፡ በአማራው ምድር ሲገባ ግን ሁኔታው እርሱ ከጠበቀው ውጪ ሆኖ አገኘው፡፡ እርሱ ሞቷል ብሎ የገመተው ኢህአፓ የተሰኘው ታሪካዊ ጠላቱ ለቀጣይ ትግሉ አደጋ ሊሆን እንደሚችል ተረዳ፡፡ ስለዚህ እርሱም እንደ ደርግ “ኢህአፓ መጥፋት ያለበት  ድርጅት ነው” በማለት ወሰነ፡፡ በወቅቱ ተጠራርጎ ሊወድቅ የሚንገታተውን የደርግ መንግሥት በአንድ ዙር ካጠናቀቀው በኋላ በኢህአፓ ላይ ለመዝመት ቆረጠ፡፡
   
    ከላይ እንደገለጽኩትም በሰኔ 1983 መጀመሪያ ላይ ከኢህአፓ ጋር የሚደረገው ጦርነት በጎጃምና በጎንደር ተጀመረ፡፡ ሚዲያው “ደርግ ወድቆ ሰላም ሰፍኗል” በሚልበት ሰዓት ጎጃምና ጎንደር በጦርነት እሳት እየተለበለቡ መሆናቸው ታወቀ፡፡ ኢህአዴጎች ስም ያልሰጡት የዚያ ዘመቻ ዓላማ “ኢህአፓ”ን ማጥፋት ሊሆን እንደሚችልም በስፋት ተወራ፡፡
   
  ጦርነቱ ቀጠለ፡፡  በደርግ ላይ በተጎናጸፈው ድል ከፍተኛ ሞራል የሰነቀው የኢህአዴግ ጦር በኢህአፓ ላይ ተረባረበ፡፡ በቁጥሩ አነስተኛ በዓላማ ጽናቱ ግን ከፍተኛ የነበረውና በአያልነሽ የሚመራው የኢህአፓ ጦር በበኩሉ የኢህአዴግን ዘመቻ ለመመከት ጥረት ማድረጉን ቀጠለ፡፡ በጦርነቱ ሳቢያ ጎጃምና ጎንደር ለእንቅስቃሴ አስቸጋሪ ሆኑ፡፡ በተለይ ደርግ ከወደቀ በኋላ አዲሱን የኢህአዴግ መንግሥት በገፍ ለመቀላቀል ይጠባበቁ የነበሩ ቀደምት የኢህአዴግ ታጋዮች፣ ከስደት ተመላሽ ምሁራንና ሌሎች የኢህአዴግ ደጋፊዎች ከሱዳን ወደ አዲስ አበባ ለመንቀሳቀስ ክፉ ፈተና ገጠማቸው (በወቅቱ የአውሮፕላን ጉዞ ተቋርጦ ስለነበር ከሱዳን ወደ አዲስ አበባ የሚኬደው በመኪና ነው)፡፡
   
    የኢህአዴግ ሰዎች ጦርነቱን በቀላሉ የሚያጠናቅቁበትን መላ ዘየዱ፡፡ በዚህም መሰረት ዋናው ጦርነት የኢህአፓ ተዋጊዎች የቆራጥነት ምልክትና የጽናት አብነት በሆነችው አያልነሽ ላይ ማተኮር እንዳለበት ወሰኑ፡፡ በመሆኑም ኮማንደር አያልነሽን ማሳደድ ጀመሩ፡፡ እርሷን ለመግደል ወይንም ከነነፍሷ ለመያዝ እንዲቻል በርካታ ልምድ ያለውን “አሉላ ክፍለ ጦር” ወደ ስፍራው ላኩ፡፡  አያልነሽና ጓዶቿም ለዘመናት ሲታገሉበት የነበረውን የኢህአፓን እስትንፋስ ለማስቀጠል የሞት ሽረት ትግል ማካሄዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ከሰኔ 1983 እስከ መስከረም 1984 ድረስ በልዩ ልዩ ስፍራዎች ከባድ ውጊያዎች ተካሄዱ፡፡ ይሁንና በብዙ እጥፍ ከሚበልጠው የኢህአዴግ ሰራዊት ጋር የተጋጠመው የኢህአፓ ሰራዊት በለስ ሳይቀናው ቀረ፡፡ በነሐሴ 1983 በጎንደር ክፍለ ሀገር ቋራ አውራጃ በተካሄደው ጦርነት እውቋ ኮማንደር አያልነሽ ከእልህ አስጨራሽ ትግል በኋላ በኢሕአዴግ ተዋጊዎች እጅ ወደቀች፡፡ በመስከረም ወር አጋማሽ የኢህአፓ መስራች አባልና ለረጅም ጊዜ የጦሩ አዛዥ የነበረው ጸጋዬ ገብረመድህን (ደብተራው) ከጥቂት ጓዶቹ ጋር ተያዘ፡፡ ከጥቅምት እስከ  ህዳር 1984 በነበረው ጊዜ ሁሉም ነገር አበቃለት፡፡ የአህአፓ ጦር ለረጅም ዘመናት ሲታገልበት ከነበረው የሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ሙሉ በሙሉ ተደመሰሰ፡፡  
     ኢህአዴግ ከጎጃምና ጎንደር የማረካቸውን የኢህአፓ ሰዎች ወደ መቀሌ እስር ቤት ወሰዳቸው፡፡ ከአራት ወራት እስር በኋላ አያልነሽና ጥቂት ሰዎች የተሐድሶ ስልጠና ተሰጥቷቸው ተለቀቁ፡፡ እነ ጸጋዬ ገብረመድህን ግን በዚያው ቀሩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ያሉበት ሁኔታ በግልጽ አይታወቅም፡፡
           *****
አያልነሽ በእስር ላይ እያለች ለአንድ ቀን በቴሌቪዥን መስኮት ታይታ ነበር፡፡ ታዲያ በወቅቱ እርሷን ያዩዋት ሰዎች መልኳ ቀደም ሲል ስለርሷ ያስቡት ከነበረው ውጪ ሲሆንባቸው በጣም ነበር የተደነቁት፡፡ “አያልነሽ” ሲባል ብዙዎች የጠበቁት ግዙፍ፤ ግድንግድ፤ ጨካኝ ፊት ያላት፤ መልከ ጥፉና አስፈሪ፣ ጎፈሬዋን ያንጨባረረች፣ ዕድሜዋ ከአርባዎቹ የሚበልጥ፣ የወታደር ልብስ የለበሰች ሴት ነበር፡፡ ሆኖም በቴሌቪዥን የታየችው አያልነሽ በግልባጩ የቀይ ዳማ፣ መለሎ፣ ዐይኖቿ እንደ ኮከብ የሚያበሩ፣ ጸጉሯ በስርዓቱ የተበጠረ፣ ሸንቃጣ ሰውነት ያላት፤ በጣም ቆንጆ የ27 ዓመት ወጣት ነበረች፡፡
                                                                                                   
  አያልነሽ ከእስር ከተለቀቀች በኋላ ለጥቂት ጊዜ በአዲስ አበባ ቆየች፡፡ በ1985 መጀመሪያ ላይ ወደ አውሮፓ ተሻግራ ሀገረ ስዊዘርላንድ ገባች፡፡ እዚያም ትዳር ከመሰረተች በኋላ የልጆች እናት ሆናለች፡፡
 
    አያልነሽ በዚያ ዘመን ስመ ገናና ነበረች፡፡ አሁንስ በምን ሁኔታ ላይ ነው ያለችው? በኔ በኩል ወሬው የለኝም፡፡ እርሷን የሚያውቋት ሰዎች ያላቸውን መረጃ ቢያካፍሉን መልካም ነው፡፡ በነገራችን ላይ ጋዜጠኛ ተስፋዬ ገብረአብ ውጪ ሄዶ ማስታወሻዎቹን ሲጽፍ ስለርሷ አንድ ነገር ይናገራል ብዬ ጠብቄ ነበር፡፡ ነገር ግን በአንድ ቦታ እንኳ የርሷን ስም አላነሳም፡፡ ከርሱ ይልቅ የቀድሞው የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ አያልነሽን በመጠኑ አስታውሰዋታል፡፡ በወቅቱ ኢህአዴግን ለመቀላቀል በሱዳን በኩል ወደ ሀገር ቤት የገቡት ዶ/ር ነጋሶ በጎንደር-አዲስ አበባ መስመር የነበረው የአያልነሽ ሰራዊት ወደ አዲስ አበባ ሊያደርጉት የነበረውን ጉዞ እንዳስተጓጎለባቸው መስክረዋል (ለማስረጃው “ዳንዲ” የተሰኘውን መጽሐፍ አንብቡት)፡፡

           *****
አያልነሽ በአጭሩ ይህቺ ነበረች፡፡ ስለርሷ የበለጠ የምታውቁ ሰዎች ያላችሁን መረጃ ልታካፍሉን ትችላላችሁ፡፡ በነገራችን ላይ የአያልነሽ የረጅም ጊዜ የትግል ጓደኛ የነበረው ገብረ እግዚአብሄር ወልደሚካኤል (ጋይም) አንዳንዶች እንደሚሉት ከአያልነሽ ጋር አልተማረከም፡፡ “ጋይም” በ1985 አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ተደብቆ በነበረበት ወቅት አንድ ውስጠ-አዋቂ ለኢህአዴግ የጸጥታ ሀይሎች ጠቆመበት፡፡ ኢህአዴጎችም እርሱን የሚይዝ አዳኝ ጦር ላኩበት፡፡ ሆኖም “ጋይም” እጁን መስጠት ስላልፈለገ ተኩስ ተከፈተ፡፡ ከ30 ደቂቃ የተኩስ ልውውጥ በኋላ ሞተ፡፡ (ስለዚህ ጉዳይ በዝርዝር ለማወቅ ካሻችሁ ሚያዚያ 1985 የታተመውን እፎይታ መጽሔት አፈላልጉ፡፡ “የኢህአፓው ኮማንደር በአዲስ አበባ” የሚል ጽሑፍ አውጥቶ ነበር)፡፡
           *****
 አፈንዲ ሙተቂ
ሸገር-አዲስ አበባ
ጥቅምት 10/2006

————-
The writer, Afendi Muteki, is a researcher of the Ethnography and History of the peoples of East Ethiopia. He is an author of “Harar Gey”, an Ethnography book about the historical city of Harar. You can read some of his articles on his facebook page.
Facebook https://www.facebook.com/afendimutekiharar


አፈንዲ ሙተቂ
—-
የአንጋፋው አርቲስት የጌታቸው ካሳ እውነተኛ ስም “ጌታቸው እሸቴ” ነበረ፡፡ ይህ አርቲስት በኪነ-ጥበቡ ተማርኮ መዘፋፈን ሲጀምር አባቱ ድምጹን በሬድዮ ይሰሙታል፡፡ አባት “ልጅህ አዝማሪ ነው” መባላቸው ክብራቸውን የሚቀንስ ሆኖ ስለተሰማቸው ልጃቸውን ያስጠሩትና እንዲህ አሉት፡፡ “ከዛሬ በኋላ ከዘፈንክ ግንባርህን በጥይት እበሳዋለሁ”፡፡

 

Salah ibn Badiya, One of the legendary Sudanese pop stars.

 ልጅ ጌታቸው ግን በአባቱ ማስፈራሪያ አላረፈረም፡፡ ከውስጡ የሚንቀለቀለው የጥበብ ዛር አላስቀምጥ ስላለው ከአባቱ እየተደበቀ ወደ ዘመኑ ክለቦችና ልዩ ልዩ መድረኮች ጎራ እያለ መዝፈኑን ቀጠለ፡፡ በዚህን ጊዜም በአንጋፋው ጋዜጠኛ ጌታቸው ደስታ ዐይን ውስጥ ገባ፡፡ ጌታቸው ደስታም ወጣቱን ድምጻዊ በሬድዮ እንዲዘፍን ጋበዘው፡፡ ነገር ግን የዘፋኙ አባት ልጃቸው በሬድዮ እንደዘፈነ ቢሰሙ በልጁ ላይ አደጋ ሊያደርሱ እንደሚችሉ ገመተ፡፡ ስለዚህ ወጣቱን ለመደበቅ እንዲቻል ስሙን “ጌታቸው ካሳ” በማለት ቀየረው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ተወዳጁ አርቲስት ላለፉት አርባ አምስት ዓመታት ጌታቸው ካሳ ተብሎ እየተጠራ ነው፡፡

*****

አንጋፋው ሱዳናዊ ድምጻዊ “ሳላሕ ኢብን ባዲያ”ም ከኛው ጌታቸው ካሳ ጋር የሚመሳሰልበት ታሪክ አለው፡፡ የሳላሕ እውነተኛ ስሙ ሳላሕ ሼኽ ሙሐመድ ነበረ፡፡ በወጣትነቱ የዘፈናቸው ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ሲተላለፉ አባቱ እሳት ጎርሰው እሳት ለብሰው መጡለት፡፡ “አንተ አዝማሪ! ልታዋርደኝ ነው የምትፈልገው?… ከዛሬ ጀምሮ በኔ ስም የምትጠራ ከሆነ እረግምሃለሁ! ውርድ ከራሴ!” በማለት አስጠነቀቁት፡፡

  ሳላሕ የአባቱን ማስጠንቀቂያ ተቀበለ፡፡ ነገር ግን የአባቱን ስም ትቶ በሐሰት ስም መጠራቱን ነፍሲያው አልቀበል አለች፡፡ አሕመድ፣ ሰይድ፣ ኢብራሂም፣ ሱፍያን በመሳሰሉት የዐረብኛ ስሞች መጠራቱ አላመችህ አለው፡፡ ማን ተብሎ ይጠራ እንግዲህ?….  አንድ ቦታ ቁጭ ብሎ ሲያሰላስል እንዲህ የሚል ሐሳብ መጣለት፡፡

  “ሳላሕ አንተ የተወለድከው በገጠር ነው አይደል?… ለምን የገጠር ልጅ ነኝ ብለህ አትጠራም?… እግረ መንገድህንም የገጠር ሰው ታላቅ ተአምር መስራት እንደሚችል ታሳይበታለህ”

ሳላሕ በድንገት ውልብ ያለበትን ሓሳብ በተግባር ላይ ሊያውለው ተነሳ፡፡ የመጀመሪያ አልበሙን ሲያሳትምም “ሳላሕ ኢብን ባዲያ” (ሳላሕ የገጠር ልጅ) የሚል ስም ተጠቀመ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለሃምሳ ዓመታት በዚህ ስም እየተጠራ ነው፡፡

*****

ሳላሕ ኢብን ባዲያ ሱዳን ካበቀለቻቸው አንጋፋ አርቲስቶች አንዱ ነው፡፡ የሱዳንን ሙዚቃ በፍቅር የሚያዳምጡ አድናቂዎቹ በተለይም እንደ ብራቅ በሚወጣው ድምጹ በጣም ይገረማሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት እድሜው ወደ ሰባዎቹ አጋማሽ ቢሆንም በአዘፋፈን ዘይቤው ላይ ምንም ድካም አይታይበትም፡፡

ከሳላሕ ኢብን ባዲያ ዘፋኖች መካከል የሀገራችን ሙዚቃ አፍቃሪያን በደንብ የሚያዉቁት “ሻዕረ ዘሐብ” የሚለውን ዜማ ይመስለኛል፡፡ በነገዋ ዕለተ ቅዳሜ ከሳላሕ ቢን ባዲያ ጋር በሓሳብ ወደ ኦምዱርማን ትበሩ ዘንድ ይህንኑ ጨዋታ ጋብዘናችኋል፡፡

(ሳላሕ “ሻዕረ ዘሐብ”ን ሲዘፍን ለማየት ይህንን የዩቲዩብ ሊንክ ይክፈቱ)

—–

አፈንዲ ሙተቂ

ታሕሳስ 4/2007

ሀረር-ምሥራቅ ኢትዮጵያ

The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history with special focus on the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his blog and his facebook page by clicking the following links


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

——
   የክፍለ ሀገር ልጅ ነኝ (በአሁኑ አጠራር የ“ክልል” ልጅ ሆኛለሁ)፡፡ የክፍለ ሀገር ልጅ መሆኔም ብዙ ጥቅም አስገኝቶልኛል፡፡ የክፍለ ሀገር ልጅ መሆኔ ቅር የሚያሰኘኝ በአንድ ነገር ብቻ ነው፡፡ ይህም በልጅነቴ የዓለም ዋንጫን በቀጥታ ስርጭት ለማየት አለመታደሌ ነው፡፡ የዚህም ምክንያት ከተማችን በዚያ ዘመን የቴሌቪዥን ስርጭት ያልነበራት መሆኑ ነው፡፡ በዚያ ዘመን በሰፊው የሀረርጌ ክፍለ ሀገር ውስጥ ከሚገኙት ከተሞች መካከል ቴሌቪዥን የነበራቸው ሀረር፣ ድሬ ዳዋ እና ጅጅጋ ብቻ ናቸው (እነዚህኛዎቹ ክፍለ ሀገር አይባሉም ማለት ነው)፡፡ ዛሬ የሳተላይ ዲሽ እንዲህ በየገጠሩ መበተኑ ላይቀር የደርግ መንግሥት ከሳተላት ዲሽ የሚከፈለውን የቀረጥ ክፍያ ከጣሪያ በላይ እየሰቀለ እኛን በመበደሉ የስራውን ይስጠው እላለሁ (ለነገሩ የአሁኑ መንግሥትም ቢሆን ከጭሮ ከተማ በስተቀር ለሌሎቹ የምስራቅ ኢትዮጵያ ከተሞች የቴሌቪዥን አንቴና አልተከለም፡፡ ኮንትሮባንድ ነው ቶሎ ከተፍ ብሎ ከልጓሙ የገላገለን!! እድሜ ለኮንትሮባንድ! እድሜ ለሀርቲሼክ መንገድ! እድሜ ለቶጎጫሌ መንገድ! ቂቂቂቂቂቂ)
    ——
   የዓለም ዋንጫ የሚባል የውድድር ዓይነት መኖሩን ያወቅኩት የማራዶና ስም በየልብሱ ላይ ታትሞ በመውጣቱ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን ከላይ በገለጽኩት ምክንያት በልጅነት ዘመኔ የተካሄዱትን ሁለት የዓለም ዋንጫዎች በቀጥታ ስርጭት ለማየት አልታደልኩም፡፡ እነርሱም የአጣሊያው የዓለም ዋንጫ (1990) እና የአሜሪካው የዓለም ዋንጫ (1994) ናቸው፡፡ (ከዚያ በፊት የነበሩት ሁለት የዓለም ዋንጫዎች እኔ ከተወለድኩ በኋላ የተካሄዱ ቢሆኑም ዕድሜዬ ገና ስለነበረ እንዳለፉኝ አድርጌ አልቆጥራቸውም)፡፡
 
   ይሁን እንጂ ሁለቱንም የዓለም ዋንጫዎች ተከታትያቸኋለሁ፡፡ የቀጥታው ስርጭት ቢያመልጠኝም ጨዋታዎቹን በሁለት ቀናት ልዩነት በቪዲዮ ካሴት እናያቸው ነበር፡፡ ለዚህ የረዳችን የሁል ጊዜ መኩሪያችን የሆነችው ድሬ ዳዋ ናት፡፡ በዚህም መሰረት ዛሬ የተካሄደው ውድድር በድሬ ዳዋ በካሴት ይቀዳና በማግስቱ ወደ ገለምሶ ከች ይላል፡፡ እኛም በሚቀጥለው ቀን ሲቻል ወደ ሀብሮ አውራጃ አኢወማ መዝናኛ ማዕከል፣ ካልተቻለ ደግሞ “ፎቶ ማወርዲ” ከሚባለው ታዋቂ ፎቶ ቤት በመሄድ ጨዋታውን እየተስገበገብን እናየዋለን፡፡ በዚህ ዓይነት በውድድሩ ከተካሄዱት ጨዋታዎች መካከል ቢያንስ ግማሽ ያህል የሚሆኑትን አይቻለሁ፡፡ ድሬ ለዚህ ባለውለታችን ናት፡፡ ማን እንደ ድሬ!! (ቀሽቲ እኮ ናት)፡፡
——–                                          
     በቪዲዮ የምናየውን ጨዋታ ውጤት በቅድሚያ እናውቀዋለን፡፡ በዚያ ላይ ደምሴ ዳምጤ በአደገኛ ምላሱ እያጣፈጠ የሚሰራቸው ዘገባዎች አያመልጡንም፡፡ የአዲስ ዘመንና የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጦችንም እንከታተላለን፡፡ በ1986 ደግሞ የግል ጋዜጦችም ተጀምረው ስለነበረ እየተሻማን እናነባቸው ነበር፡፡ ታዲያ ይህ ሁሉ ቅድመ-መረጃ በቪዲዮ የተቀዳልንን ጨዋታ ጣዕም አያደፈርስብንም፡፡ እንዲያውም ደምሴ በዘገባው የጠቀሳቸውን ነጥቦች በጨዋታው ውስጥ ለመመልከት ስንል በከፍተኛ ተመስጦ ውስጥ እንገባለን፡፡
  ታዲያ ዘወትር የሚገርመኝ አንድ ነገር አለ፡፡ ያለፉትን አምስት የዓለም ዋንጫዎችን በቀጥታ ስርጭት ነው ያየኋቸው (እግር ኳስን በቀጥታ ማየት የጀመርኩት እንደኛ አቆጣጠር በ1988 በተካሄደው የEuro-96 ወቅት ነው፡፡) ቢሆንም እነዚህ በቀጥታ ስርጭት ያየኋቸው ጨዋታዎች ያኔ በቪዲዮ እየተቀዱ ከሁለት ቀናት በኋላ የምናያቸውን ጨዋታዎች ያህል አይጣፍጡኝም፡፡ ጎሉም ሆነ ጨዋታው፣ ተጫዋቹም ሆነ ቡድኖቹ፣ አሰልጣኙም ሆነ ዳኛው ያኔ በልብ ላይ ይቀራል፡፡ ከዚያ ወዲህ ግን ሁሉም ነገር ተለውጧል፡፡ በተለይም ባለፉት ሁለት የዓለም ዋንጫዎች ካየኋቸው ክስተቶች አንዳቸውም በአዕምሮዬ ውስጥ የሉም፡፡ ውጤቱንም ብትጠይቁኝ ልነግራችሁ አልችልም (እ.ኤ.አ በ2006 በተካሄደው የዓለም ዋንጫ ዚነዲን ዚዳን ካሳየው ጣፋጭ ፉት ቦልና በፍጻሜው ጨዋታ ማቴራዚን በቴስታ ደረቱ ላይ መቶት ከመጣሉ ውጪ ማለቴ ነው)፡፡
በዚህ ጽሑፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁትን የዓለም ዋንጫ አስቃኛችኋለሁ፡፡ የአሜሪካውን የዓለም ዋንጫ በሌላ ጽሐፍ እመጣበታለሁ፡፡
==== 14ኛው የዓለም ዋንጫ በኢጣሊያ (Italy-1990)===
በኢጣሊያ የተካሄደው 14ኛው የዓለም ዋንጫ በእግር ኳስ ኤክስፐርቶች በጣም አሰልቺ የተባለለት ነው፡፡ በያንዳንዱ ውድድር የገቡት ጎሎች በአማካይ ከሁለት አይበልጡም፡፡ ቢሆንም ግን ያኔ ሁሉም ነገር እየጣፈጠን ነው ያየነው፡፡ ለኛ አሰልቺና አስቀያሚ የሆነብን የመጨረሻው ጨዋታ ብቻ ነው፡፡ በዚያ ጨዋታ ዳኛው ብዙ ቢጫና ቀይ ካርዶችን ማሳየታቸው ሳያንሰን አጨቃጫቂ “ሪጎሬ” ሰጥተው የጨዋታውን ስሜት አበላሹብን፡፡
  በዚያ የዓለም ዋንጫ የተካሄዱትን ጨዋታዎች በተመለከተ ዝርዝር ዘገባውን ከኢንተርኔት ስለምታገኙት እዚያ ውስጥ አልገባም፡፡ እኔ እዚህ የማደርገው ከአዕምሮዬ ያልጠፉ ክስተቶችንና ስብዕናዎች ማሳወቅ ነው፡፡
·        አስደሳቹ መጽሐፍ  
በውድድሩ ዋዜማ በጣም ተወዳጅ የሆነ አንድ መጽሐፍ ታትሞ ነበር፡፡ ርዕሱ “እግር ኳስ፤ ፊፋ እና የዓለም ዋንጫ” ይሰኛል፡፡ በአማርኛ ቋንቋ በስፖርት ዙሪያ ከተዘጋጁ መጻሕፍት እንደርሱ የሚማርከኝ የለም፡፡ ያ መጽሐፍ በርካቶቻችን እግር ኳስን እንድንወደው አስተዋጽኦ ያደረገ ይመስለኛል፡፡ በዓለም ዋንጫውን በንቃት እንድንመለከት ያስቻሉን መረጃዎችንም ሰጥቶናል፡፡ ያንን መጽሐፍ ያዘጋጁት የአዲስ ዘመን ጋዜጣ የስፖርት አምድ አዘጋጆች የነበሩት ግርማ ሰይፉ እና ፋንታሁን ሀይሌ ናቸው፡፡
ታዲያ ያ መጽሐፍ በአንድ ነገር አቀዣብሮኛል፡፡ መጽሐፉ በዝርዝር የሚያወሳቸውን እውቅ ተጫዋቾች በዓለም ዋንጫው ላይ የማያቸው መስሎኝ በጉጉት ስጠብቃቸው ነበር፡፡ በተለይም በ13ኛው የዓለም ዋንጫ ወቅት የተጫወቱትን ተጫዋቾች በናፍቆት እየጠበቅኳቸው ነው ውድድሩ የተጀመረው፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ የውሃ ሽታ ሆነው ቀሩ፡፡ ጥቂቶቹ ብቻ (ማራዶና፣ ቡርቻጋ፣ ቫንባስተን፣ ሩድ ጉሌት፣ ካሬካ፣ ጋሪ ሊነከር፤ ጆን ባርነስ፣ ሎታር ማትያስ፣ ሩዲ ቮለር ) በውድድሩ ውስጥ ነበሩ፡፡ የብራዚሉን ፓውሎ ሮቤርቶ ፋልካኦን ደግሞ ለተጫዋችነት ስጠብቀው አሰልጣኝ ሆኖ አገኘሁት፡፡
·        የአጂፕ ኩባኒያ ውለታ፡
ጨዋታው በጣሊያን ሀገር የተካሄደ በመሆኑ በኢትዮጵያ ውስጥ ስርጭቱን ለማስተላለፍ ስፖንሰር የሆነው የኢጣሊያ ኩባኒያ የሆነው አንጋፋው ነዳጅ አቅራቢ “አጂፕ” ነው፡፡ ያኔ በየጨዋታው መሀል ሲነገር ከነበረው ማስታወቂያ እንደሰማሁት “አጂፕ” በኢትዮጵያ ውስጥ 120 የማደያ ጣቢያዎች ነበሩት፡፡ እስከ አሁን ድረስ ቢኖር ኖሮ 1200 ጣቢያዎች ሳይኖሩት ይቀራል?  
·        የካሜሩን ጉዞ

በዓለም ዋንጫው እጅግ ከፍተኛ ደስታ የፈጠረልን የካሜሩን አስደናቂ ጀብድ ነው፡፡ አርጀንቲናን፣ ሩማኒያንና ኮሎምቢያን ያሸነፈባቸው ጨዋታዎች ከማንም አዕምሮ ውስጥ አይጠፉም፡፡ ሮጀር ሚላ፣ ኦማም ቢይክ፣ ማካናኪ እና በረኛው ቶማስ ንኮኖ የዘወትር ትዝታዎቻችን ናቸው፡፡ ይሁንና ለዋንጫው በጉጉት ስንጠብቀው የነበረው ያ አስደሳች ቡድን በእንግሊዝ ጉድ ተሰራና ከመንገድ ላይ ቀረብን፡፡
ያ ጨዋታ ከፍተኛ የዳኛ ተጽእኖ የታየበት መሆኑ አሌ አይባልም፡፡ ካሜሩን እንግሊዝን በሁለት ለአንድ እየመራ ወደ መጨረሻው ደረሰ፡፡ ጨዋታው ሊጠናቀቅ ስምንት ደቂቃ ብቻ ሲቀረው ዳኛው የፍጹም ቅጣት ምት ለእንግሊዝ ሰጡ፡፡ በዚህም እኩል ሆኑ፡፡ በጭማሪው ሰዓትም ዳኛው በድጋሚ ለእንግሊዝ ሪጎሬ ሰጡና አፍሪቃዊያንን የባሰ አሳረሩ፡፡ ተቃጠልን ነው የምላችሁ!! በጣም ሚያሳርረው ደግሞ እነዚያን ሁለት ከይሲ ጎሎች ያስቆጠረው ከላይ የጠቀስኩትን መጽሐፍ አንብቤ በጉጉት ስጠብቃቸው ከነበሩት ተጫዋቾች አንዱ የነበረው እንግሊዛዊው ጋሪ ሊነከር መሆኑ ነው (ጋሪ ሊነከር በሜክሲኮ በተካሄደው 13ኛው የዓለም ዋንጫ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ ነው የጨረሰው)፡፡
   ለኳስ እንደዚያ የተናደድኩበት ጊዜ የለም፡፡ ከኔ በላይ ደግሞ ኳስ አፍቃሪው ኢትዮጵያዊ ህዝብ እርር ነው ያለው፡፡ ታዲያ ጨዋታውን በቪዲዮ ማየት እንደጀመርን (“ቪዲዮው ተቀድቶ የሚመጣልን የጨዋታው ውጤት ከታወቀ በኋላ ነው” ያልኳችሁን አትዘንጉ) ማን እንደፈጠረው የማይታወቅ ወሬ በከተማችን ተዛምቶ ነበር፡፡ “ዳኛው ተጽእኖ ያደረገ መሆኑ ስለተረጋገጠ ጨዋታው ይደገማል” የሚል፡፡ ይህ ወሬ እውነት ነው ብለን ስንጠብቅ ከሁለት ቀን በኋላ እንግሊዝ ከጀርመን ጋር ትጫወታለች ተብሎ ተነገረ፡፡ እንደገና እርር!! እንደገና መቃጠል!! ደግነቱ ጀርመንና ጣሊያን እንግሊዝን ቀጥተውልናል፡፡
·        የማይረሱ ጨዋታዎች
የዓለም ዋንጫው የግብ ድርቅ ስላጠቃው “ወዝ የለውም” ይባል እንጂ ዘወትር ከሰው ህሊና የማይጠፉ ምርጥ ጨዋታዎችንም አይተንበታል፡፡ አርጀንቲናና ሩማኒያ፣ ካሜሩንና ኮሎምቢያ፣ ጀርመንና ኮሎምቢያ፣ ኢጣሊያና ቼኮዝሎቫኪያ፣ ብራዚልና ስዊድን፤ አርጀንቲና እና ኢጣሊያ፣ ጀርመንና ሆላንድ፣ አየርላንድና ሩማኒያ በጣም ጥሩ ጨዋታ አሳይተውናል፡፡
·        እጅግ ምርጥ ጨዋታ
ከላይ ከጠቀስኳቸው ጨዋታዎች ይበልጥ ሁሉንም ሰው ቁጭ ብድግ ያደረገው የአርጀንቲናና ብራዚል ጨዋታ ይመስለኛል፡፡ ከምድቡ ሶስቱንም ጨዋታዎች በአሸናፊነት ያጠናቀቀው ብራዚል ካሜሩንን እንኳ ማሸነፍ ባቃተው የአርጀንቲና ቡድን ተረታ፡፡ ለዋንጫ የጠበቅነው ቡድን ስለነበረ ልባችን ነው የተቆረጠው፡፡
·         አስደሳች ተጫዋቾች
 የሩማኒያው ጆርጅ ሃጂ፣ የአርጀንቲናዎቹ ዲየጎ ማራዶና እና ክላውዶ ካኒንጃ፣ የካሜሩኖቹ ሮጀር ሚላ እና ማካናኒ፣ የብራዚሎቹ ካሬካ፣ አሊማው እና ሙለር፣ የኢጣሊያዎቹ ሳልቫቶሬ ሺላቺ እና ሮቤርቶ ባጂዮ፣ የቼኮዝሎቫኪያው ቶማስ ስኩራቪ፣ የስፔኑ ሚሼል፣ የእንግሊዞቹ ጋሪ ሊነከር እና ፖል ጋስኮኝ፣ የእንግሊዙ በረኛ ፒተር ሼልተን፣ የጀርመኖቹ ሎታር ማትያስ እና ሩዲ ቮለር በጣም ምርጥ ተጫዋቾች ነበሩ፡፡  

·        የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች
በዚያ የዓለም ዋንጫ ላይ ካየኋቸው ተጫዋቾች መካከል ኮከብ ነው ብዬ የምመርጠው የኮሎምቢያውን ካርሎስ ቫልዴራማን ነው፤ በለው! በለው! አቤት ጨዋታ! አቤት ታክቲክ! አቤት አብዶ መስራት፣ ወይኔ! ወይኔ! (ወደዳችሁም ጠላችሁም ኳስ ድሮ ቀረ አቦ!)
ቫልዴራማ ኳስ ሲይዝ አስማት በሉት! ሜዳው ጠቦት ይሸከረክርበታል፡፡ በተለይም የጀርመን ተጫዋቾችን እያጥበረበረ ሲያታልላቸው ሁኔታው ሁሉ ነፍስ ግቢ ነፍስ ውጪ ሆኖባቸው ነበር፡፡ የካሜሩን ቡድንም ኮሎምቢያን አሸንፎ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ የቻለው በረኛው ቀሽም በመሆኑ እንጂ በኮሎምቢያ ቡድን ድክመት አይደለም፡፡ ቫልዴራማ በዚያ ጨዋታም ላይ ኮከብ ሆኖ ነበር የዋለው፡፡ ቫልዴራማ እ.ኤ.አ. በ1987 የላቲን አሜሪካ ኮከብ ተጫዋች ተብሎ ተመርጦ ነበር (በ1986 ኮከብ የሆነውን ማራዶናን በልጦ ማለት ነው)፡፡
·        ምርጥ ወጣት ተጫዋቾች
በዚያን ጊዜ ለጨዋታው ልጅ እግር ከሆኑት መካከል በጣም ያስደሰቱኝ ሁለት ወጣቶች ናቸው፡፡ አንደኛው የስዊድኑ ቶማስ ብሮሊን ነው፡፡ ቡድኑ ሁሉንም ጨዋታዎች ተሸንፎ ከምድቡ ቢባረርም ብሮሊን በአጨዋወቱ ማንንም ነበር ያስደሰተው፡፡ ደግሞም በብራዚል ላይ አንድ ግብ አስቆጥራል (ብሮሊን በቀጣዩ የዓለም ዋንጫ ሶስተኛ ኮከብ ሆኗል)፡፡
   ሌላኛው የኢጣሊያው ሮቤርቶ ባጅዮ ነው፡፡ ሮቤ ለኢጣሊያ ሁለት ጎሎችን በማስቆጠር አያያዙ አደገኛ መሆኑን አስመሰክሯል፡፡ እነዚህ ሁለት ተጫዋቾች በኢጣሊያው “ሴሪ አ” ተገናኝተው ምርጥ ፉት ቦል አሳይተውናል፡፡
·        የማይረሱ ተጫዋቾች
1.      ሬኔ ሂጉታ፡
የኮሎምቢያ በረኛ ነው፡፡ በሁኔታዎቹ ሁሉ እብድ በሉት፡፡ ኳስ በእግሩ እንጂ በእጁ ለመያዝ ይጠየፋል፡፡ ሲያቀብል በእግር! ሲቀበልም በእግር! በዚያ ሁኔታው ኮሎምቢያ ለሁለተኛው ዙር ማለፉ አስደናቂ ነበር፡፡ የሂጉታን እብደት ያጠናው የካሜሩኑ ሮጀር ሚላ ግን ሳያስበው ጉድ ሰራው፡፡ አቤት የያኔው የአፍሪካ ደስታ! አቤት የሚላ ዳንስ!! (አቤት የደምሴ ዳምጤ አዘጋገብ)!
2.     የአርጀንቲናው በረኛ፡
ስሙን ዘንግቼዋለሁ፡፡ ሁለተኛ በረኛ ሆኖ ነበር ወደ ኢጣሊያ የሄደው፡፡ ነገር ግን ዋናው በረኛ ከሶቪየት ህብረት ጋር በተደረገው ጨዋታ በመጎዳቱ እርሱን ተክቶ ወደ ጨዋታው ገባ፡፡ ከዚያ በኋላ ማን ይቻለው!!? በተለይም ኢጣሊያ በደጋፊዎቿ ፊት ተጫውታ በመለያ ምቶች በአርጀንቲና ስትሸነፍ የበረኛው አስተዋጽኦ ሌላ ነው፡፡ (ያኔ የውድድሩ ኮከብ በረኛ ምርጫ ባይደረግም ከሁሉም የሚበልጠው እርሱ ይመስለኛል)፡፡   
·        ምርጥ ግብ አዳኞች
1.      ቶማስ ስኩራቪ (ቼኮዝሎቫኪያ)፡
በሁለተኛው ዙር በኮስታሪካ ላይ የሰራውን ሀትሪክን ጨምሮ አምስት ጎሎችን ነው ያስቆጠረው፡፡ ሁለቱን ጎሎች ያስቆጠረው ቼኮዝሎቫኪያ አሜሪካን 5-1 ባሸነፈችበት ጨዋታ ነው፡፡ በዚያን ጊዜ ቼኮዝሎቫኪያ አሜሪካን ማሸነፏ ሶሻሊዝም በኢምፔሪያሊዝም ላይ የተጎናጸፈው ድል ተደርጎ ስለተወሰደ የአውራጃችን አኢወማ መሪዎች ከደስታ ብዛት ማበድ ነው የቀራቸው (ትልቋ ሶቪየት ህብረት በአርጀንቲና መሸነፏን ያልሰሙ ይመስል ጉራው ሌላ ነበረ)፡፡
  ፖለቲካው ሌላ ነው፡፡ ቶማስ ስኩራቪ ግን ያለምንም ማጋነን ነፍስ የሆነ ተጫዋች ነበረ፡፡ ጎል ለማግባት የተፈጠረ አጥቂ ነው፡፡ ይሁንና ከዚያ የዓለም ዋንጫ በኋላ በድጋሚ አላየሁትም (እነ ጆርጅ ሃጂንና ካርሎስ ቫልዴራማን ግን በድጋሚ ለማየት ችለናል)፡፡
2.     ሚሼል (ስፔን)
በጣም ጎበዝ አጥቂ ነበር፡፡ በምድብ ማጣሪያው በደቡብ ኮሪያ ላይ ሀትሪክ ሰርቷል፡፡ በቤልጅግም ላይ አንድ ግብ አስቆጥሯል፡፡
3.     ካሬካ  እና ሙለር (ብራዚል)፡
 አቤት ጨዋታ! አቤት ፍጥነት!! አቤት ዳንስ! በህይወቴ ካየኋቸው አስደሳች ተጫዋቾች መካከል ናቸው፡፡ ሁለቱም በጥምረት የሚያጠቁ ሲሆን ብራዚል ያስቆጠረቻቸውን አራት ግቦች ያገቡት እነርሱ ናቸው፡፡
    ካሬካ በስዊዲን  ላይ ሁለት ጎሎችን ካስቆጠረ በኋላ በቢጫ ማሊያው የደነሰው “ሳንባ” ዳንስ መቼም ቢሆን የሚረሳኝ አይሆንም፡፡ አስራ አንድ ቀጥሩ ሙለርም በኮስታሪካና በስኮትላንድ ላይ አንዳንድ ግቦችን አስቆጥሮ ቡድኑን ወደ ሁለተኛው ዙር አሸጋግሮታል፡፡
4.     ሮጀር ሚላ (ካሜሩን)፡
 ዓለም በሙሉ ነበር የተደነቀበት፡፡ በዓለም ዋንጫ በ38 ዓመቱ ተሰልፎ ከአዕምሮ የማይጠፉ ግቦችን ለማስቆጠር የቻለ ሰው እርሱ ብቻ ይመስለኛል (ይህ ሪከርድ ከአራት ዓመት በኋላ በራሱ ተሰብሯል)፡፡ የሚደንቀው ነገር ሮጀር ሚላ ግቦቹን ያገባው ከእረፍት በኋላ ተቀይሮ እየገባ ነው፡፡ በሩማኒያ እና ኮሎምቢያ ላይ ሁለት ሁለት ጎሎችን ካስቆጠረ በኋላ የደነሰው ዳንስ የሁሉም አፍሪቃዊ ትዝታ ነው (ደምሴ ዳምጤ ጨዋታዎቹን ሲዘግባቸው አፍ ያስከፍት ነበር)፡፡ ታዲያ እስከ አሁን ድረስ ያልገባኝ ነገር ሰውዬው ሮጀር ሚላ ሆኖ ቴሌቭዥኑ “ሚለር” (Miller) እያለ የሚጠራው መሆኑ ነው፡፡
5.     ሳልቫቶሬ ሺላቺ (ኢጣሊያ)
አስገራሚ ብቻ ሳይሆን የዘረኝነትን መጋረጃ የደመሰሰ ተጫዋች ነው፡፡ በሲሲሊ ደሴት ላይ ከምትገኘው የፓሌርሞ ከተማ ተወልዶ የሀብታሞቹን የሰሜን ኢጣሊያ ልጆች ለመብለጥ የቻለ ነው፡፡ ከሰሜናዊ ኢጣሊያ ከተሞች (ሚላን፣ ቶሪኖ፣ ሮማ፣ ፍሎሬንስ፣ ቬኒስ፣ ወዘተ…) የተገኙ ሰዎች በነርሱ እይታ “ደሀ” የሚባሉትን የሲሲሊና የሳርዲኒያ ሰዎችን ያለ ልክ ይንቋቸዋል፡፡ በሁሉም ነገር አንደኛ እኛ ነን ይላሉ፡፡ ሺላቺ ግን ሳይወዱት በግድ ወደ ውስጣቸው እንዲመለከቱ አደረጋቸው፡፡
  
  ይህ ተጫዋች ኢጣሊያ ባደረገቻቸው ሰባት ግጥሚያዎች ላይ ስድስት ግብ አስቆጥሯል፡፡ በዚህም የውድድሩ ኮከብ ግብ አግቢ በመሆን የወርቅ ጫማ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ ይሁንና ከውድድሩ በኋላ በኢጣሊያ ውስጥ በዘላቂነት ሊጫወት አልቻለም፡፡ ለረጅም ጊዜ ከኢጣሊያ ተሰዶ ለጃፓን ቡድኖች ይጫወት እንደበረ አውቃለሁ፡፡ አሁን ምን ላይ እንደደረሰ አላውቅም፡፡
  
·        የማይረሱ ጎሎች
1.      ከሮጀር ሚላ ጎሎች መካከል በሬኔ ሂጉታ ላይ ያስቆጠራት ሁለተኛዋ ጎል በዓለም የፉትቦል ተመልካቾች ዘንድ ዘወትር የምትታወስ ትመስለኛለች፡፡
2.     የቼኮዝሎቫኪያው ቶማስ ስኩራቪ በኮስታሪካ ላይ ያስቆጠራቸው ሶስት ጎሎችም አይረሱም፡፡
3.     የአርጀንቲናው ክላውዶ ካኒንጃ ብራዚልን ከጨዋታ ውጪ ያደረገችውን ጎል አስቆጥሮ ስንቱን አስለቀሰ?… ወይኔ ብራዚል! እንደዚያ ምርጥ ጨዋታ እየተጫወተ በመንገድ ላይ ቀረብን!
4.     የኮሎምቢያው ፍሬዲ ሪንኮን በጀርመን ላይ ያስቆጠራት ግብ ፈጽሞ አትረሳም፡፡ ያ ጨዋታ ግብ አልባ ሆኖ ወደ መጠናቀቁ ሲቃረብ ጀርመኖች በ88ኛው ደቂቃ ላይ አንድ ጎል አገቡ፡፡ በዚህም ኮሎምቢያ ያለቀለት መሰለ፡፡ ከዓለም ዋንጫ ሊባረር የሚባረርበት ጊዜ ቀረበ፡፡ ነገር ግን ካርሎስ ቫልዴራማ ብልሃቱን አምጥቶ ያገኛትን ኳስ አስተካክሎ ለፍሬዲ ሬንኮን አቀበለ፡፡ ሬንኮንም የአቻነቷን ጎል አስቆጠረ፡፡ ኮሎምቢያም በአንደኛው ዙር ከመባረር ተርፋ ወደ ቀጣዩ ዙር አለፈች፡፡
·        ኮከብ አሰልጣኝ
የጀርመኑ ፍራንዝ ቤከንባወር ኮከብ አሰልጣኝ ሆኖ መመረጡ ትክክል ይመስለኛል፡፡ ቡድኑ አንድም ጨዋታ ሳይሸነፍ ለዋንጫ ደርሶለታልና፡፡ እኛም ጀግናውን ቤከንባወርን በተጫዋችነት ዘመኑ ለማየት ባይቻለንም በአሰልጣኝነቱ በማየታችን እድለኞች ነን፡፡
·       የማይረሳው አሰልጣኝ
የአርጀንቲና አሰልጣኝ ካርሎስ ቢላርዶን ማንም የሚረሳው አይመስለኝም፡፡ ቢላርዶ ከሌሎቹ አሰልጣኞች የሚለይበት ነገር አሰልጣኞች ከሚቀመጡበት ወንበር ላይ በመነሳት ወደ ሜዳው እየሄደ ለተጫዋቾቹ እየጮኸ ምክር ቢጤ የሚለግስ መሆኑ ነው፡፡ ያኔ በተመለከትኳቸው ጨዋታዎች ሁሉ አሰልጣኞች ከወንበራቸው ሲነሱ አላየኋቸውም፡፡ ካርሎስ ቢላርዶ ግን ከተጫዋቾቹ እኩል ነበር የሚንቀሳቀሰው፡፡
በቀጣዮቹ የዓለም ዋንጫዎች ግን ያ ልማድ ተቀየረ፡፡ ሁሉም አሰልጣኝ ከወንበር እየተነሳ የሚመክር በመሆኑ ወንበር ላይ ተቀምጦ ጨዋታውን የሚያይ አሰልጣኝ ጠፋ (እኔ እንደታዘብኩት ከዚያ ወዲህ ካየኋቸው አሰልጣኞች መካከል ጨዋታው ከተጀመረ በኋላ የተለየ እንቅስቃሴ የማያሳዩት የሞሮኮ ቡድንን ለረጅም ጊዜ ሲያሰልጥኑ የነበሩት ሄንሪ ሚሼል እና በ2002 የኮሪያ-ጃፓን የዓለም ዋንጫ ሴኔጋልን ያሰለጠኑት ብሩኖ ሚትሱ ናቸው፡፡ ( ሄንሪ ሚሼል ቁጭ ብሎ ማስቲካውን ያኝካል፤ ጎል ከገባበት ግን ይናደድና ሲጋራውን ያቀጣጥላል፤ ብሩኖ ሚትሱ ደግሞ እጆቻቸውን በማጣመር ይቆሙና ይተክዛሉ)፡፡  
·        የጨዋታው ማስታወሻ
የዓለም ዋንጫው ከተጠናቀቀ በኋላ ብሄራዊ ሎተሪ ውድድሩን አጠቃልሎ የሚዘግብ ፖስተር በማሳተም አስደሰተን፡፡ የፖስተሩ አብዛኛው ክፍል ለሩብ ፍጻሜ የደረሱትን ስምንት ቡድኖችና የውድድሩ ቅመሞች የነበሩትን ምርጥ ተጫዋቾች በፎቶግራፍ ያሳያል፡፡ ከታች ደግሞ በውድድሩ የተከናወኑ ጨዋታዎች ውጤት በሰንጠረዥ ተጠቃልሎ ቀርቧል፡፡ ብሄራዊ ሎተሪ ፖስተሩን በነጻ ለማሰራጨት ያዘጋጀው ይመስለኛል፡፡ ይሁን እንጂ ለማንም ሰው በነጻ ሲሰጥ አላየሁም፡፡ ሁሉም ሰው በብር እየገዛው ነው በቤቱ ሲለጥፈው የነበረው፡፡ ያ ልምድ በቀጣዩ የዓለም ዋንጫም ተደግሟል፡፡ በዚህ ዘመን ያለው አሰራር ግን ሌላ ነው፡፡ የውድድሩን ፕሮግራሞች ለማሳየት በሚል ከጨዋታው በፊት የተዘጋጁ እንጂ የዓለም ዋንጫ ከተጠናቀቀ በኋላ የሚዘጋጅ የማስታወሻ ፖስተር አላየሁም፡፡

Read more ›


(አፈንዲ ሙተቂ)
——
አሁንም ግን እደግመዋለሁ!! እኔ ህልመኛ ነኝ! ይህ የኔ ህልም በፈጣሪም ሆነ በሰው ልጆች ዘንድ “ብሩክ” ተብሎ የሚወደስ ነው፡፡ ስለህዝቦች ፍቅር፣ ህብረት፣ አንድነትና እኩልነት ማለም የዘወትር ተግባሬ ነው፡፡ መቼም ቢሆን ይህንን ከማድረግ ወደ ኋላ አልልም፡፡ እንኳንስ በደንብ የማውቃቸውን የኤርትራና የኢትዮጵያ ህዝቦችን ይቅርና አምስቱ የምስራቅ አፍሪቃ ሀገራት (ሱዳን፣ ኢትዮጵያ፣ ሶማሊያ፣ ጅቡቲና ኤርትራ) በኮሎኒያሊስቶች የተሰመሩ ድንበሮችን በጣጥሰው በአንድ ግዛት ስር እንዲጠቃለሉ በጽኑ አልማለሁ፡፡ ምን ይሄ ብቻ! ትልቋ እማማ አፍሪቃም አንድ ሀገር እንድትሆን በብርቱ ነው የማልመው፡፡
*****
ኤርትራና ኢትዮጵያ ሰው ሰራሽ ችግሮች በቆሰቆሷቸው አቧራዎች መነሾነት ሁለት ሀገር ሆነዋል፡፡ ፍቺያችን በደም የታጀበ መሆኑ በጣም ያሳዝነናል፡፡ ያስለቅሰናል፡፡ ይህ ማለት ግን “አንድ ላይ የመሆናችን ጉዳይ ለዘልዓለሙ አብቅቶለታል” ማለት አይደለም፡፡ ሰው ሰራሽ ድንበር በኛ መካከል ቢሰመርም ባህል፣ ታሪክ፣ ቋንቋና ጂኦግራፊ በአንድ ላይ ያስተሳስረናል፡፡ የህዝቦቻችን የጋራ ታሪካዊ ውቅር መቼም ቢሆን አይፋቅም፡፡ 
  እኛና ኤርትራዊያን በጣም ነው የምንመሳሰለው፡፡ እንዲህ የሚመሳሰሉ ህዝቦች የማታ ማታ ተመልሰው አንድ የሚሆኑበትን ሁኔታ የዓለም ታሪክ አሳይቶናል፡፡ ሁለቱ ጀርመኖች ከአርባ አምስት ዓመታት በኋላ ተዋህደዋል፡፡ ሁለቱ የመኖችም ከሰላሣ ዓመታት በኋላ ሲዋሃዱ አይተናል፡፡ ታዲያ ይህንን እያየን የምን ተስፋ መቁረጥ ነው?
   እኛና ኤርትራዊያን ከመመሳሰልም አልፎ በጣም ነው የምንቀራረበው፡፡ በጣም እንዋደዳለን፡፡ ይህንን በቀላሉ ለመረዳት ኤርትራዊያንና ኢትዮጵያዊያን በዲያስፖራው ክፍለ-ዓለም የሚኖሩበትን ሁኔታ ማስተዋል ይበቃል፡፡ ወደየትኛውም የዓለም ሀገር ሄደን ብናይ ከማንም በላይ ለኤርትራዊያን የሚቀርቡት ኢትዮጵያዊያን ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ለኢትዮጵያዊያንም ከማንም በላይ የሚቀርቡት ኤርትራዊያን ናቸው፡፡ አምና (በህዳር ወር 2005) የሳዑዲ ዐረቢያ የጸጥታ ሀይሎች በኢትዮጵያዊያን ላይ የወሰዱትን በደልና ግፍ የተቀላቀላበትን ከሀገር የማባረር እርምጃ ከኢትዮጵያዊያን ጎን ቆመው ሲያወግዙ የነበሩት ኤርትራዊያን ብቻ ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያዊያን ባካሄዷቸው ሰልፎች ላይ ከኤርትራዊያን በስተቀር የሌላ ሀገር ዜጋ አልተሳፈተም፡፡
  
   የሜዲትራኒያን ባህርን በህገ-ወጥ ጀልባዎች በማቆራረጥ ወደ አውሮጳ ሲከንፉ ባህሩ የሚበላቸው ኢትዮጵያዊያንና ኤርትራዊያን ምንዱባንስ እንዴት ይረሳሉ?… ስለነርሱ በምንሰማው መጥፎ ዜና ሁለታችንም አንድ ላይ “እህ!” እያልንና በቁጭት እየተቃጠልን አይደለም እንዴ?… መርዶአቸው በአንድ ላይ እየደረሰን በአንድ ላይ ለቅሶ እየተቀመጥን አይደለም እንዴ?…
በደጉም ቢሆን መመሳሰላችንና መፈቃቀራችን ብዙ የተጻፈለት፣ ብዙ የተነገረለት ነው፡፡ ዛሬም ድረስ ያንን ሳቂታ የቤኒ አምር ወጣት የኛ ልጅ በመሆኑ ነው የምናውቀው፡፡ ዛሬም ድረስ ከኤርትራዊ ጎረቤቶቻችን ጋር ፋሲካና አረፋን በአንድነት እንታደማለን፡፡
*****
  እኛ ኤርትራን የምንፈልጋት ለወደቦቿ ስንል አይደለም፡፡ እኛ ኤርትራን የምንፈልገው ሁለመናዋ ከኛ ጋር ስለሚመሳሰልና አንድ ዓይነት ስለሆንን ነው፡፡ እኛ ኤርትራን የምንፈልገው ከነህዝቧ ነው፡፡ የኤርትራ ህዝብ የኛ ህዝብ ነው፡፡ እኛ ራሳችን የኤርትራ ህዝብ ነን፡፡ ኤርትራም ኢትዮጵያ ናት፤ ኢትዮጵያም ኤርትራ ናት፡፡ ኤርትራ ወደብ ባይኖራት እንኳ ይህ አቋማችን አይቀየርም፡፡ ታሪኳ፣ ባህሏ እና ቋንቋዋ እናንተ ከምታውቁት ተቀይሯል እስካልተባለ ድረስ ስለርሷ ማለማችንን አንተውም፡፡
 
  ህልማችን ጽኑ ነው፡፡ ወደፊት የትግበራ ምዕራፎቹን እያሰፋ የሚሄድ ነው እንጂ በእንጭጩ ተቀጭቶ የሚቀር አይደለም፡፡ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም በአፋቤት ሽንፈት ሲያጋጥማቸው በተስፋ መቁረጥ ስሜት “ቤንዚን አይቆፈርበት፤ አልማዝ አይወጣበት፣ ሰው የለበት! Nothing`” እንዳሉት እኛም ተስፋ ቆርጠን ኤርትራንና ህዝቧን የምናጥላላበት ሁኔታ በፍጹም አይከሰትም፡፡ ቢኢዝኒላህ!! ኢንሻ አላህ!!
   እኛ ስለትልቋ ኤርትራ ማለምን ትተን “አሰብ የኢትዮጵያ ወደብ ናት” ከሚሉት የወደብ ጥማተኞች ጎንም አንሰለፍም፡፡ ፍላጎታችን “የኢኮኖሚ እድገት” በሚባለው የማቴሪያሊስቶች ዝባዝንኬ የሚመራ ባለመሆኑ ለጥቅም ብለን ህልማችንን በመንደር ደረጃ አናሳንሰውም፡፡ ቢኢዝኒላህ!!
   
    የእነዚህን የወደብ ጥማተኞች ቅስም ለመስበር በሚል የፖለቲካ ስሌት ተነሳስተን “የአሰብ ወደብ እጣ ፈንታ የግመሎች ውሃ መጠጫ ኩሬ ከመሆን አያልፍም” የሚል ታሪካዊ ተወቃሽነትን የሚያስከትል ቃልም አይወጣንም፡፡ ቢኢዝኒላህ!!
 
  እኛ ኤርትራዊያንን እንደኛው አድርገን ነው የምናያቸው እንጂ አንዳንድ ብስጩዎች በሚተነፍሷው ወሬዎች ተናደን “የቅኝ-ተገዥነት ስሜት ሰለባዎች ናችሁ” በማለት አንፈርጃቸውም፡፡ በምንም መልኩ ቢሆን ኤርትራዊ ወገናችንን የሚያሳቅቅና የሚያበሳጭ ክፉ ንግግር አንናገርም፤ ክፋታችንንና የውስጥ ጥላቻችንን የሚያሳብቅ ጽሑፍም አንጽፍም፡፡ በውስጣችን ስለኤርትራ መውደም እያሰብን በምላሳችን ብቻ “አንድ ህዝቦች ነን” እያልን የምንሰብክ መናፍቃንም አይደለንም፡፡ እኛ ኤርትራንና ህዝቧን የምንወደው ከልባችን ነው፡፡ ስለነርሱ የምናልመው ህልማችንም ከልባችን ከተወረወረ የፍቅር ፍላጻ የፈነጠቀ ነው፡፡
*****
ህልማችን የቅርብ ሳይሆን የሩቅ ነው! እጅግ በጣም ሩቅ!! ይሁንና ርቀቱን ፈርተን ማለማችንን አንተውም፡፡ ዘወትር ስለውቢቷ ኤርትራና ህዝቧ ማለማችንን እንቀጥላለን!! ከሩቁና መልከ-መልካሙ ህልማችን ጋር ወደፊት!!
—-
አፈንዲ ሙተቂ
ጳጉሜ 4/2006
—-
Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia. You may follow him on his facebook page. Just click this link


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–

ዕለቱ መስከረም 2/1977 ነበር፡፡ በዚያች ዕለት ደርግ ከአጼ ኃይለሥላሤ መንግሥት ስልጣን የተረከበበት 10ኛው የአብዮት በዓል ይከበር ነበር፡፡ ያ በዓል ከቀደሙት በዓላት ለየት የሚልበት አንድ ነገር ታይቶበታል፡፡ ይህም የስመገናናው የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ (ኢሠፓ) ምስረታ በይፋ መታወጅ ነው፡፡ ይህንን ድርብ ደስታ ለማድመቅ ተብሎ የተዘጋጀው ክብረ በዓል በሀገራችን ታሪክ በድጋሚ አልታየም፡፡ ለዚህ በዓል ማክበሪያ በትንሹ አንድ መቶ ሚሊዮን ብር ወጪ ሆኗል (ያ ገንዘብ በአሁኑ ስሌት ሁለት ቢሊዮን ብር ሊሆን ይችላል)፡፡

በዚያን ጊዜ ነው በአስራ ዘጠኝ ሚሊዮን ብር የተሰራው ታላቁ የኢሠፓ የጉባኤ አዳራሽ ተመርቆ የተከፈተው፡፡ ከጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ፊት ለፊት ያለው የ“ትግላችን” ሀውልትም በዚህ በዓል ወቅት ነው የተመረቀው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ለበዓሉ የታጨችው አዲስ አበባ በደማቅ መብራቶችና በልዩ ልዩ መፈክሮች ተጥለቅልቃ ነበር፡፡ እንግዶች በሚንቀሳቀሱባቸው ዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ ያሉ አሮጌ ቤቶች በግንብ አጥርና በትላልቅ የጨርቅ ሽፋኖች እንዲከለሉ ተደርገዋል፡፡ የክፍለ ሀገር ዋና ከተሞችና የአውራጃ ከተሞችም በመፈክሮችና በማጭድና መዶሻ ምስሎች አሸብርቀዋል፡፡ በዋና ዋና መንገዶች ላይ ያሉ የንግድ ድርጅቶችና የመንግሥት መስሪያ ቤቶች በሶስት ቀለማት (አረንጓዴ፤ ቢጫ፤ ቀይ) የተዘጋጁ አምፖሎችን እንዲያበሩ ታዘዋል፡፡ በየቀበሌው የተቋቋሙ የኪነት ቡድኖችም ኢሠፓን የሚያወድሱ መዝሙሮችን አፍልቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የነጭና ጥቁር ስርጭቱን ትቶ ወደ ሙሉ የቀለም ስርጭት የተሸጋገረው በዚያች ታሪካዊ ዕለት ነው፡፡

በዚያ ታላቅ ክብረ በዓል ላይ የምስራቅ ጀርመን ኮሚኒስት ፓርቲ ዋና ፀሐፊና የሀገሪቱ መሪ የነበሩትን ጓድ ኤሪኽ ሆኔከርንና የየመን ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ (ደቡብ የመን) መሪ ጓድ ዓሊ ናስር አል-ሐሰንን ጨምሮ በርካታ የሶሻሊስት ሀገራት ልዑካን ተገኝተዋል፡፡ ከአፍሪቃም የዛምቢያው ኬኔት ካውንዳ፤ የዚምባብዌው ሮበርት ሙጋቤና የሞዛምቢኩ ጓድ ሳሞራ ማሼል የበዓሉ ታዳሚ ነበሩ፡፡ ዋናው የበዓሉ አከባበር ስነ-ስርዓት በኢሠፓ ጉባኤ አዳራሽና በአብዮት አደባባይ የተካሄደ ሲሆን በተለይም በአብዮት አደባባይ የተካሄደው ልዩ ትርዒትና ወታደራዊ ሰልፍ በሀገሪቱ ታሪክ ተወዳዳሪ አልተገኘለትም፡፡
*****
“ኢሠፓ” የሚባለው ዝነኛ ፓርቲ የተመሰረተው ለአምስት ዓመታት የዘለቀ መጠነ ሰፊ ዝግጅት ከተደረገ በኋላ ነው፡፡ ለፓርቲው ምስረታ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን እንዲያቀላጥፍና ህዝቡን በሶሻሊስታዊ ስርዓት እንዲያደራጅ በሚል “የኢትዮጵያ ሰርቶ አደሮች ፓርቲ አደራጅ ኮሚሽን” (ኢሠፓአኮ) የተባለ ከፍተኛ የአስፈጻሚ አካል በመስከረም 1972 ተመስርቶ ነበር፡፡ ይህንን ኮሚሽን ማቋቋሙ ያስፈለገው “የሰርቶ አደሩን ፓርቲ ለመመስረት የሚቻለው ህዝቡን በማንቃትና በማደራጀት በአንድ ማዕከል ዙሪያ ካሰባሰቡ በኋላ ነው ” በሚለው የኮሚኒስቶች ርዕዮተ-ዓለማዊ መርህ መሰረት ነው፡፡ የዚህ ኮሚሽን ተጠሪ በመሆን በየክፍለ ሀገሩ የተመደቡ ወኪሎች የየአካባቢው የበላይ ውሳኔ ሰጪዎች ነበሩ፡፡ የኮሚሽኑን ዓላማ የሚገልጸው “የኢሠፓአኮ ተልዕኮ ይሳካል” የተሰኘ መፈክር በመላው ኢትዮጵያ ተደጋግሞ ይሰማ ነበር፡፡
  ኢሠፓ የተመሰረተው ለአምስት ቀናት በተካሄደ መስራች ጉባዔ ነው፡፡ በጉባኤው ማጠቃለያ ላይ በድርጅታዊ አሰራር የተዘጋጀ ምርጫ ተደረገ፡፡ ጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም የፓርቲው ዋና ጸሐፊ ሆነው መመረጣቸውም ተነገረ፡፡ ከርሳቸው ጋርም መቶ ሰማኒያ ሶስት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ተመረጡ፡፡
*****
የኢሠፓ አወቃቀርና አሠራር በሌሎች የሶሻሊስት ሀገራት ከታዩት ኮሚኒስት ፓርቲዎች ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ፓርቲው የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት የበላይ ነው፡፡ የፓርቲውና የአስፈጻሚ አካላቱ ግንኙነት የጎንዮሽ ሳይሆን ከላይ ወደታች የተዘረጋ መዋቅራዊ መልክ ነበረው፡፡ በመሆኑም ኢሠፓ በየትኛውም እርከን ላይ ላሉት አስፈጻሚ አካላት የበላይና አመራር ሰጪ ነው፡፡ ይህ አወቃቀር በሀገር አቀፍ፣ በክፍለ ሀገርና በአውራጃ ደረጃ የተዘረጋ ነው፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ የነበሩት የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች አመራር የሚቀበሉት ከኢሠፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽ/ቤት ነው፡፡ በክፍለ ሀገርና በአውራጃ ደረጃ ያሉ መስሪያ ቤቶችም ከኢሠፓ ጽ/ቤት ነው አመራር የሚሰጣቸው፡፡ በመሆኑም የአውራጃና የክፍለ ሀገር የኢሠፓ ኮሚቴ አንደኛ ፀሐፊ ሆኖ የተመደበ ሰው በፕሮቶኮልም ሆነ በስልጣኑ ከሌሎች ተሿሚዎች ሁሉ ይበልጣል፡፡
 የኢሠፓ መዋቅር በኢ-መደበኛ ሁኔታ ሁሉንም የመንግሥት መስሪያ ቤቶች አዳርሷል፡፡ በያንዳንዱ የመንግሥት መስሪያ ቤት፣  በማምረቻና ማከፋፈያ ድርጅቶችና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ “የኢሠፓ መሰረታዊ ድርጅት ጽ/ቤት” የሚባል መምሪያ ነበረ፡፡ የዚህ መሰረታዊ ድርጅት ዓላማ የኢሠፓን ርዕዮተ ዓለም ማስተማርና ከበላይ አካል የመጡ መመሪያዎች ተፈጻሚ መሆናቸውን መቆጣጠር ነው፡፡ ለፓርቲ አባልነት ብቁ የሆኑ ጓዶችን መልምሎ የአባልነት መታወቂያ የሚሰጠውም እርሱ ነው፡፡
ኢሠፓ በፕሮፓጋንዳው ዘርፍ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ያደርግ ነበር፡፡ የፓርቲው ልሳን “ሠርቶ አደር” የሚባለው ሳምንታዊ ጋዜጣ ነው፡፡  መስከረም ደግሞ የፓርቲው የርዕዮተ ዓለም መጽሔት ነው፡፡ የፓርቲው አባላት በሁለቱ ህትመቶች በወጡ ጽሑፎች ላይ የመወያየት ግዴታ አለባቸው፡፡
 ኢሠፓ የደርግ መንግሥት ከስልጣን እስከተወገደበት ጊዜ ድረስ ቆይቷል፡፡ በስልጣን ላይ በነበረባቸው ሰባት ዓመታት በጠቅላላው ከ100, 000 ያላነሱ አባላትን አፍርቷል፡፡ አባላቱ ከሲቪልም ሆነ ከጦር ሀይሉ ክፍል የተመለመሉ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ የፓርቲ አባል በስራ ቀናት ከካኪ የተሰፋ ሱሪና ኮት የመልበስ ግዴታ አለበት (ይህ መመሪያ የወጣው “የሀገር ውስጥ ምርቶችን ማበረታታት አለብን” በሚል መነሻ ነው፤ ካኪው በቃሊቲ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ነው የሚመረተው)፡፡ 
ከላይ እንደገለጽኩት የኢሠፓ ዋና ፀሐፊ ጓድ መንግሥቱ ኃይለ ማሪያም ነበሩ፡፡ ፓርቲው ምክትል ዋና ፀሐፊ በይፋ ባይሰይምም የጓድ መንግሥቱ ተከታይ ሆነው ሲሰሩ የነበሩት ጓድ ፍቅረ ሥላሤ ወግደረስ ናቸው፡፡ የርዕዮተ-ዓለም መምሪያ ሃላፊው ጓድ ሽመልስ ማዘንጊያ ሲሆኑ ጓድ ብርሃኑ ባይህ የውጭ ግንኙነት መምሪያ ሃላፊ ነበሩ፡፡ ጓድ ሸዋንዳኝ በለጠ የኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ሃላፊ፤ ጓድ ተካ ቱሉ የኦዲትና ቁጥጥር ኮሚሽን ሃላፊ፣ ጓድ ደበላ ዲንሳ የማህበራዊ ጉዳዮች መምሪያ ሃላፊ፣ ጓድ ሜጀር ጄኔራል ገብረየስ ወልደሃና የወታደራዊ ጉዳዮች መምሪያ ሃላፊ ነበሩ፡፡ ከሁሉም በላይ ስልጣናቸው ገንኖ የነበረው  ግን የድርጅት መምሪያ ሃላፊው ጓድ ለገሠ አስፋው ናቸው፡፡
  *****
ኢሠፓ የምስረታ ጉባኤውን በሚያካሄድበት ወቅት (ጳጉሜ1-ጳጉሜ 5/1976) ሀገሪቱ በከፍተኛ ድርቅ ተጠቅታ ነበር፡፡ ከአምስት ሚሊዮን የማያንሱ ዜጎች በትግራይ፣ በወሎ፣ በጎንደር፣ በኤርትራ፣ በሀረርጌና በባሌ ክፍላተ ሀገር በቸነፈር ተጠብሰው በሞት አፋፍ ላይ ነበሩ፡፡ አንዳንድ የሀገር ተቆርቋሪዎች መንግሥት የፓርቲ ምስረታ ጉባኤውን ለሌላ ጊዜ እንዲያስተላልፍና የ10ኛ አብዮት በዓልን እንዲያስቀር ቢወተውቱም ሰሚ አላገኙም፡፡ የወቅቱ መንግሥት የድርቁ መኖር ከታወቀ በአብዮት በዓል አከባበሩ ላይ ጥላውን ያጠላል በማለት የምዕራብ ሀገራት የዜና አውታሮች ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገቡ ከልክሎአቸው ነበር፡፡ ይሁንና አንዳንድ ሚዲያዎች የዜና ዘጋቢዎቻቸውንና የቪዲዮ ሪፖርተሮቻቸውን በድብቅ ወደ ሀገር ውስጥ በማስረግ የዓለም ህዝብ አስከፊውን ድርቅ እንዲያየው አድርገዋል፡፡ በነዚያ ሪፖርተሮች የተቀረጹ ምስሎችን የተመለከቱ የዓለም ህዝቦች ለድርቅ የተጋለጠውን ኢትዮጵያዊ ረሀብተኛ ለመታደግ በተንቀሳቅሰዋል (በሰር ቦብ ጊልዶፍ አስተባባሪነት የተሰባሰቡ የዓለማችን እውቅ አርቲስቶች Live Aid የተባለውን የሙዚቃ ዝግጅት ያቀረቡት ያኔ ነው፡፡ አርቲስቶቹ በዝግጅቱ ላይ በጋራ ያዜሙት We are the world የተሰኘው ዜማ ከምንጊዜም ምርጥ ዜማዎች መካከል አንዱ ሆኖ ተመዝግቧል)፡፡
   የደርግ መንግሥት በህጋዊ መንገድ ፈቅዶላቸው የመጡ ጥቂት የሶሻሊስት ሀገራት ዘጋቢዎች ደግሞ “ድርቅ በመቶ ሺህ የሚቆጠር ህዝብ እየቀጠፈ ለዚህ በዓል ከፍተኛ በጀት መመደብ አግባብ ነውን?” የሚል ጥያቄ በይፋ በማቅረብ የሀገሪቱን ከፍተኛ ባለስልጣናት አጨናንቀዋል፡፡ በመሆኑም የአብዮት በዓሉ ሲፈጸም መንግሥት በድርቅ የተጎዳውን ህዝብ ለመታደግ መንቀሳቀሱ ግድ ሆኖበታል፡፡ ሆኖም የመንግሥት እርምጃ በጣም የዘገየ በመሆኑ አምስት መቶ ሺህ የሚሆኑ ኢትዮጵያዊያን በዚያ አስከፊ ድርቅ አልቀዋል፡፡
—–
አፈንዲ ሙተቂ
መስከረም 2/2007


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
ብዙዎቻችን በስርቅርቅ ድምጻቸው እናውቃቸዋለን፡፡ እጅግ በተዋጣለት የኦርኬስትራ ቅንብር በመታጀብ የተጫወቷቸው ጥዑም ዜማዎች  በአዕምሮአችን ላይ ተቀርጸዋል፡፡ እኔ ጸሐፊው ሙዚቃቸውን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁበትን አጋጣሚ አላስታውስም፡፡ ሆኖም የነርሱን ዘፈን በምሰማበት ጊዜ ሁሉ ሶስት ነገሮች ይታወሱኛል፡፡
   የመጀመሪያው ከተማችንን (ገለምሶን) ለሁለት ከፍሎ የሚያልፈውን አውራ ጎዳና ተከትለው ከተደረደሩት ሻይ ቤቶች ይንቆርቆር የነበረው የእንስቶቹ ዝማሬ ነው፡፡ በተለይም የሻይ ቤቶቹ ባለቤቶች በበርካታ የህብረተሰብ ክፍል እንደ ህብረ-ዜማ ይዘፈን የነበረውን “መሼና መሼና”ን እየደጋገሙ ማጫወታቸው የየዕለቱ ትዕይንት ሆኖ እንደቆየ አስታውሳለሁ፡፡ ሁለተኛው አይረሴ አጋጣሚ የተከሰተው በትምህርት ቤት ቆይታዬ ነው፡፡ በ1980 የአምስተኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ ከለገዳዲ ሬድዮ ጣቢያ የሚተላለፈውን “የህብረተሰብ ትምህርት በሬድዮ” ለማዳመጥ በሄድንበት አንድ ጠዋት “ተማሪዎች፤ የኢትዮጵያ ጎረቤት የሆነችውን ሱዳንን ታውቋታላችሁ?” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ትምህርት ተሰጠን፡፡ የሬድዮ ትምህርቱን የሚያቀርበው ባለሙያ “ሱዳን፣ በአፍሪቃ ትልቅ ሀገር ናት፤ ስፋቷ ወደ አንድ ሚሊዮን ስኩዌር ማይልስ ይጠጋል፤ ዋና ከተማዋ ካርቱም ነው” እያለ በሚያስተምርበት ጊዜ በየአፍታው እንደመሸጋገሪያ አድርጎ የተጠቀመው እንስቶቹ “ለውነል መንጋ” እያሉ የሚያዜሙትን ተወዳጅ ዘፈን ነበር፡፡ ያንን ዘፈን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት በዚያች ዕለት ነው፤ ከዚያ በኋላ ከጭንቅላቴ ላወጣው አልቻልኩም፡፡
  ሶስተኛው አጋጣሚ በ1984 በአንዲት የማክሰኞ ምሽት ነው የተከሰተው፡፡ በዕለተ ማክሰኞ ሲገበያይ የሚውለው የከተማችን ህዝብ የቀኑን ድካም ለማራገፍ ሲል ምሽት ላይ እራቱን ከበላ በኋላ ሆጃና ሻይ አፍልቶ ለበርጫ መሰየሙ የተለመደ ነገር ነው፡፡ እኔም በዚያች የማክሰኞ ምሽት አብዱልቃዲር ከተባለ ዘመዳችን ሱቅ ሄድኩና ከጥቂት ጓደኞቹ ጋር በርጫውን ሲያስኬድ አኘሁት፡፡ አብዱልቃዲር ለበርጫው ማሟሟቂያ የመረጠው የእንስቶቹን ተወዳጅ ካሴት ነው፡፡ በተለይም ደግሞ “ኡሸ ሰጊራ፣ ኪፋያ ዐለይና” የተሰኘውን ዘፈን ይደጋግመው ነበር፡፡ እኔም የአብዱልቃዲር ሁናቴ አስገርሞኝ ስለእንስቶቹ እንዲያጫውተኝ ጠየቅኩት፡፡ እርሱም የዘፋኞቹን ማንነትና የሙዚቃ ጉዞአቸውን እያዳነቀ ተረከልኝ፡፡ እንግዲህ በዚያች አጋጣሚ ነው ስማቸውን ለመያዝ የበቃሁት፡፡
*****
አዎን! የኢትዮጵያን ሙዚቃ አውቃለሁ የሚል ሰው ሶስቱን የሱዳን ድምጻዊያን በደንብ ነው የሚያውቃቸው፡፡ እነዚህ እንስቶች እህትማማቾች ናቸው፡፡ ትክክለኛ ስማቸውም “ሐያት”፣ “አመል” እና “ሃዲያ” ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ በደንብ የሚታወቁት ግን “አል-በላቢል” በተሰኘው የቡድን ስማቸው ነው (በዐረብኛ “አል-ባቢል” ሲባል “ዘማሪ ወፎች” እንደማለት ነው)፡፡ በምስራቅ አፍሪቃ የሙዚቃ ታሪክ የነርሱን ያህል የሚታወቅ የሴት ድምጻዊያን ቡድን የለም፡፡
“አል-በላቢል” በሰሜን ሱዳን በዋዲ-ሃልፋ ከተማ ነው የተወለዱት ነው፡፡ የአፍ-መፍቻ ቋንቋቸው “ኑቢያ” ነው፡፡ ሙዚቃን በዋዲ ሃልፋ ቢጀምሩትም ከእውቅና ማማ ላይ የወጡት ግን በካርቱም ከተማ ነው፡፡ በተለይም እንስቶቹ እ.ኤ.አ ከ1974-እስከ 1982 በነበረው ዘመን በሱዳን ሙዚቃ ላይ ነግሰው ነበር፡፡ በዚያ ዘመን ያወጧቸው “መሼና”፣ “ሙትዓሉ ዐለይና”፣ “ሸባብ አንኒል”፣ “ዑሸ ሰጊራ”፤ “ለውነል መንጋ”፣ “ሒልዊን ሐለዋ”፣ “ጣኢረል ጀንና” የመሳሰሉት ዘፈኖቻቸው ዘመን ተሻግረው እስከ ዛሬም ድረስ ይደመጣሉ፡፡
  የአል-በላቢል አዕዋፋት ዝና በምድረ-ሱዳን ብቻ አልታቀበም፡፡ ከካይሮ እስከ ሞምባሳ፣ ከበርበራ እስከ ባማኮ (ማሊ) ባሉት የአፍሪቃ ከተሞች የሚኖሩ የሙዚቃ አፍቃሪዎች በስራቸው ተማርከውላቸዋል፡፡ በኢትዮጵያ፣ በግብጽ፣ በሶማሊያ፣ በጅቡቲ፣ በቻድ፣ በኬንያ፣ በናይጄሪያ፣ በአልጄሪያ፣ በማሊና በሌሎችም የአፍሪቃ ሀገራት ሙዚቃዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ፣ በአውሮጳና በአሜሪካም ተዟዙረዋል፡፡
*****
ሆኖም ሶስቱ እንስት ከ1986 በኋላ የሙዚቃ ስራቸውን በአንድ ላይ ለመቀጠል አልቻሉም፡፡ ትልቋ “ሐያት” እና ሁለተኛዋ ሃዲያ በጋብቻ ምክንያት ሱዳንን በመልቀቃቸው ብዙዎች ያደነቁላቸው የቡድን ስራቸው በመንገድ ላይ ቀረ (ሐያት በአሜሪካ፣ ሐዲያ ደግሞ በባህሬን ይኖሩ ነበር)፡፡ ሆኖም የሱዳን ህዝብ እንዲሁ አልተዋቸውም፡፡ እንስቶቹ በአንድ ላይ ተሰባስበው ስራቸውን እንዲሰሩ በልዩ ልዩ መንገድ ጫና ሲያደርግባቸው ነበር፡፡ እነርሱም ለህዝቡ ውዴታ በመሸነፋቸው በድጋሚ በመሰባሰብ የሙዚቃ ስራቸውን ማቅረብ ጀምረዋል፡፡
    ታዲያ አል-በላቢል በድጋሚ የቡድን ስራቸውን በጀመሩበት የአውሮጳዊያኑ 1998 አጋማሽ ላይ የለቀቁት “ኩልለ-ኑጁም” የተሰኘው አልበም በዓለም ዙሪያ በእልፍ አዕላፍ ቅጂዎች ነው የተሸጠው፡፡ የሱዳን የሙዚቃ ኤክስፐርቶች በዚያ አልበም የተካተቱትን ስራዎች ከሀገሪቱ የምንጊዜም ተወዳጅ ዜማዎች መካከል ደምረዋል፡፡ በተለይም የአልበሙ መጠሪያ የሆነው “ኩልላ-ኑጁም” የተባለው ዜማ ከሱዳን አልፎ በውጪው ዓለም (በጀርመን) ለሽልማት አብቅቶአቸዋል፡፡ የአውሮጳ ህብረት በበኩሉ ታህሳስ 11/ 2013 ባዘጋጀው ልዩ ዝግጅት እህትማማቾቹ ለሱዳን ሙዚቃ እድገት ላደረጉት አስተዋጽኦ ዓለም አቀፍ ሽልማት ሸልሞአቸዋል፡፡ እንስቶቹ የምታዩትን ፎቶግራፍ የተነሱት ሽልማቱን በተቀበሉበት ወቅት ነው፡፡
*****
አል-በላቢልን በሌላ ቀን እንዘይራቸዋለን፡፡ ለዛሬ ግን በኛ ሀገር በስፋት የሚታወቀውን “መሼና”ን እንገባበዝና እናብቃ፡፡
 መሼና መሼና መሼና
ቢጠሪቀል ሑብቢ መሼና
አዕዛቡ ያ ናር አልጊና
መሼና መሼና መሼና…
(እህትማማቾቹ መሼናን ሲዘፍኑ ለማየት የሚከተለውን ሊንክ ይክፈቱ)፡፡
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 4/2007
ገለምሶ-ምስራቅ ኢትዮጵያ
—-
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


(አፈንዲ ሙተቂ)
——
በኢትዮጵያ የታሪክ ሂደት የተፈጠሩ የፖለቲካ ድርጅቶችና ሽምቅ ተዋጊ ቡድኖች በትግል ዘመናቸው ከወደቁ ሰማዕቶቻቸው ሁሉ አግዝፈው የሚመለከቱት አንዳንድ ጀግና አላቸው፡፡ ለምሳሌ የተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ ( ጀብሃ) ትልቁ ሰማዕት “ዑመር እዛዝ” ይባላል፡፡ የህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) ታላቅ ሰማዕት ደግሞ “ኢብራሂም አፋ” ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ) ትልቁ ሰማዕት “ተስፋዬ ደበሳይ” ነው፡፡ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) “ታላቁ ሰማዕት” ኤሌሞ ቂልጡ ይባላል፡፡ የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አባላት በበኩላቸው እንደ ትልቁ ሰማዕት የሚያዩት ሃየሎም አርኣያን ነው፡፡
Hayelom Ar’aya
  ታዲያ ሃየሎም ከሌሎቹ ሰማዕታት የሚለይበት አንድ ጠባይ አለ፡፡ ይህም በጀግንነቱ በህወሓት ብቻ ሳይሆን የህወሓት ቀንደኛ ጠላት በሚባሉ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር የሚወደስ መሆኑ ነው፡፡ እርግጥ ስለሃየሎም ጀግንነት በስፋት መጻፍ የጀመረው እርሱ ከተገደለ በኋላ ነው፡፡ ሆኖም ሃየሎም በህይወት እያለ እንኳ ስለጀግንነቱ ሲሰጡ የነበሩ የምስክርነት ቃሎችን በልዩ ልዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ አንብበናል፡፡ ለምሳሌ የቀድሞው የኢህዴን ሊቀመንበር ያሬድ ጥበቡ (ጌታቸው ጀቤሳ) “መስታወት” በተሰኘ መጽሔት ላይ በጻፉት አንድ ጽሑፍ ሁሉንም የኢህአዴግ መሪዎች በፈሪነት ከፈረጇቸው በኋላ ሃየሎም አርኣያን ብቻ በጀግንነት አወድሰዋል፡፡ በኤርትራና በትግራይ ሲዋጉ የነበሩ የደርግ የጦር መኮንኖችም በተለያዩ መጽሔቶች ስለሃየሎም ኣርኣያ ጀግንነት ሲያወሱ ነበር፡፡
 በመሆኑም በሃየሎም የጦር ሜዳ ጀግንነትና በወታደራዊ ጥበብ አዋቂነቱ ላይ ጥርጣሬ የሚቀርብ አይመስለኝም፡፡ ሆኖም የሃየሎምን አሟሟት ያየ ሰው “ሰውዬው ሰማዕት ነው ሊባል ይችላልን?” የሚል ጥያቄ ሊያቀርብ ይችላል፡፡ ምክንያቱም በተለምዶ ሰማዕታት የሚባሉት በትግሉ ሂደት ሲዋጉ የወደቁ ሰዎች ናቸውና፡፡ ሃየሎም የተገደለው ግን የትጥቅ ትግሉ ካበቃ ከአራት ዓመታት በኋላ በተከሰተ ጸብ ነው፡፡
 የኢህአዴግ ሰዎች “ሃየሎም በሰላም ጊዜ በሚደረገው ትግል መሃል የወደቀ ጓዳችን በመሆኑ ሰማዕት ነው” እንደሚሉ ይታወቃል፡፡ ከሰማዕታቱ መካከል የተናጥል ሃውልት ያቆሙትም ለርሱም ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ወገኖችስ በሰማእትነቱ ላይ ምን ይላሉ? በጉዳዩ ላይ ያላቸውን አቋም እንዲነግሩን እንጠብቃለን፡፡
*****
ሃየሎም አርኣያ ህወሓት (በኋላም ኢህአዴግ) ባካሄዳቸው ዋና ዋና ዘመቻዎች ላይ የመሪነት ሚና ነበረው፡፡ ከነዚያ ዘመቻዎች መካከል ከስሙ ጋር ተቆራኝቶ የቀረው በየካቲት ወር 1978 የተካሄደው “ኦፕሬሽን አግአዚ” ነው፡፡ ይህንን ኦፕሬሽን የሚመለከት ጽሑፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነበብኩት በሚያዚያ 1985 በታተመው “እፎይታ” መጽሔት ላይ ነው፡፡ ተራኪው ደግሞ ሃየሎም አርኣያ ራሱ ነበረ፡፡
 ታዲያ ጽሑፉ በጣም የሚያስደምም በመሆኑ ብዙዎች ታሪኩን በመጠራጠር “ሰውዬው የተናገረው ልብወለድ ነው እንጂ እውነተኛ ነገር  አይደለም” ብለው ነበር፡፡ በዘመኑ ከኢህአዴግ በታቃራኒነት የተሰለፉት የደርግ ከፍተኛ ባለስልጣናት “ኦፕሬሽን አግአዚ” በትክክል የተፈጸመ ዘመቻ መሆኑን መናገር ሲጀምሩ ግን የሃየሎም ትረካ እውነተኛት ሊረጋገጥ በቅቷል፡፡ በዚህ ረገድ የመጀመሪያውን ምስክርነት የሰጡት ጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም እራሳቸው ናቸው (በ1994 የታተመውን የሌ/ኮ/ መንግሥቱ ኃይለማሪያም ትዝታዎችን ያስታውሱ)፡፡ በማስከተልም “ነበር” የተሰኘውን ተወዳጅ መጽሐፍ የጻፉት ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ) “ኦፕሬሽን አግአዚ” በትክክል መፈጸሙን አረጋግጠዋል፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡
   “ኦፕሬሽን አግአዚ” በመቀሌ እስር ቤት ታስረው የነበሩ ከሶስት ሺህ የሚበልጡ የህወሐት ታጋዮችንና ደጋፊዎችን የማስለቀቅ ተልዕኮ ነበረው (ኦፕሬሽኑ የተሰየመለት “አግዓዚ” የሚባለው ታጋይ ከህወሐት መስራቾች አንዱ ነው፤ “አግዓዚ” የትግል ስሙ ሲሆን እውነተኛ ስሙ “ዘርዑ ገሠሠ” ነበር)፡፡ እንደ ጄኔራል ሃየሎም አርኣያ አገላለጽ ኦፕሬሽኑን ለማካሄድ የሚያስፈልገው ቅድመ ዝግጅት ለስድስት ወራት ያህል ተካሄዷል፡፡ በኦፕሬሽኑ የሚሳተፉ ኮማንዲስቶች በሚስጢር ነው የሰለጠኑት፡፡ ሆኖም ሰልጣኞቹ በስልጠናው ላይ በነበሩበት ወቅት ስለኦፕሬሽኑ ምንም መረጃ አልነበራቸውም፡፡ በመሆኑም እነዚያ ሰልጣኞች ለስልጠናው ወደተዘጋጁት የአሸዋ ቤቶች በሚወሰዱበት ጊዜ ከፊሉ “ይህ የመቀሌ ቤተ መንግሥት ነው” ይሉ የነበረ ሲሆን የተቀሩት ደግሞ “አይ! የአየር ማረፊያው ነው” እያሉ ልዩ ልዩ መላምቶችን ይደረድሩ ነበር፡፡
  “ኦፕሬሽን አግአዚ” በታቀደለት ጊዜ ተካሄደ፡፡ የህወሓት አሸማቂዎችም ማንም ባልጠበቀው ሁኔታ ወደ መቀሌ እስር ቤት በመግባት የሚፈልጓቸውን ታሳሪዎች በሙሉ አስለቀቁ፡፡ በማግስቱ ወሬው በአዲስ አበባ ሲሰማ በሊቀመንበር መንግሥቱና በጦር ጄኔራሎቻቸው ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ ተቀሰቀሰ፡፡ መቀሌ ያሉ የጦር መሪዎችም ለአስቸኳይ ግምገማ ተጠሩ፡፡ በግምገማው ማብቂያም “ለኦፕሬሽኑ መሳካት ትልቁን ሚና የተጫወተው በአካባቢው የነበረው አብዮታዊ ጦር አዛዥ የነበረው ብ/ጄኔራል ታሪኩ ዐይኔ ያሳየው እንዝህላልነት ነው” ተባለ፡፡
  የደርግ መንግሥት ባለስልጣናት ታሪኩን ሲጽፉ “የህወሓት ጦር በእስር ቤቱ ላይ ወረራ በፈጸመበት ወቅት የእስር ቤቱ ሃላፊ ወደ ጄኔራል ታሪኩ በመደወል “በወንበዴ ተወርሬአለው፤ ባሉኝ ጠባቂዎች መከላከል ስለማልችል ረዳት ጦር በአስቸኳይ ይላኩልኝ” በማለት ሲጠይቀው ጄኔራል ታሪኩ “እኔ መደበኛ ወታደር እንጂ የእስር ቤት ጠባቂ ዘበኛ አይደለሁም” የሚል የሹፈት መልስ ሰጥቶት ከቤቱ ገብቶ ተኝቷል፤ የአንድ አብታዊ ጦር ዋና ዓላማ ሀገሩን ከውጭ ወራሪዎችና ከውስጥ ወንበዴዎች መከላከል ሆኖ ሳለ ጄኔራል ታሪኩ ረዳት ጦር ለወህኒ ቤቱ እንዳይደርስ በማድረጉ ወያኔ ታሳሪዎቹን በቀላሉ ለማስመለጥ ችሏል፤ በዚህም ጄኔራሉ የወንበዴዎቹ ዓላማ ተባባሪ ሆኗል” ይላሉ፡፡
 በተለይ ግን ጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም “ኦፕሬሽን አግአዚ”ን በምሬት ነው የሚያነሱት፡፡ ጓድ መንግሥቱ “ወያኔ በዚያ ድንገተኛ ወረራ ሊያመልጡ የማይገባቸውን ወንጀለኞች ለማስለቀቅ ችሏል” በማለት ለጋዜጠኛ ገነት አየለ አንበሴ ነግረዋታል፡፡ ሆኖም ለወንበዴዎቹ ድጋፍ ሰጥተዋል በተባሉት ጄኔራል ታሪኩ ዐይኔ ላይ መጥፎ እርምጃ አልተወሰደም፡፡ ጓድ መንግሥቱ ይህንንም ሲያብራሩ “የታሪኩ ጓደኛ የሆኑ የጦር መሪዎች በአማላጅነት ወደኔ መጥተው “ጓድ ሊቀመንበር! ታሪኩን በዚሁ ብቻ ከምንመዝነው ወደ ኤርትራ ይላክና ችሎታውን ያሳይ” ስላሉኝ እኔም ቃላቸውን በመቀበል ወደ አፋቤት ልኬዋለሁ” ብለዋል (ሆኖም ጄኔራል ታሪኩ ወደ አፋቤት ቢቀየርም ከአራት ዓመታት በኋላ ተረሽኗል)፡፡
እነ ሃየሎም አርኣያ በበኩላቸው በጄኔራል ታሪኩ ላይ የቀረበውን ክስ አይቀበሉም፡፡ ሃየሎም ስለጉዳዩ ሲናገር “ጄኔራሉ ጦሩን ለማንቀሳቀስ ያልቻለው በእንዝህላልነት ሳይሆን የኛ ጦር በመቀሌ ከተማ የተለያዩ ስፍራዎች የማዘናጊያ ውጊያዎችን በመክፈቱ መደበኛው ወታደር በነዚያ ውጊያዎች ስለተወጠረ ነው፤ እኛም የማዘናጊያ ውጊያዎቹን ሽፋን በማድረግ ያለምንም ስጋት እስረኞቹን ለማስለቀቅ ችለናል” ብሏል፡፡ 
   “ኦፕሬሽ አግዓዚ”ን በተመለከተ አከራካሪ ሆኖ የዘለቀ አንድ ጉዳይ አለ፡፡ ይህም ኦፕሬሽኑን ለማካሄድ የወሰደውን ጊዜ የሚመለከት ነው፡፡ ጄኔራል ሃየሎም አርኣያ “ኦፕሬሽኑ የተካሄደው በአስራ አምስት ደቂቃ ውስጥ ነው፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ስራችንን ሙሉ በሙሉ መጨረስ እንደምንችል ያወቅነው ስልጠናው በሚካሄድበት ወቅት ነው” ብሏል፡፡ የደርግ ባለስልጣናት ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ዘርዘር ያለ ነገር ባይጽፉም ኦፕሬሽኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ መፈጸሙን በደፈናው ያምናሉ፡፡  (በነገራችን ላይ የ“ኦፕሬሽን አግአዚ”ን ታሪክ መሰረት ያደረጉ ሁለት ፊልሞች ተሰርተዋል፤ አንደኛውን ፊልም ያዘጋጀው ታዋቂው አርቲስት ኪሮስ ኃይለ ሥላሤ ሲሆን የሁለተኛውን ፊልም አዘጋጅ ማንነት በትክክል አላውቅም፤ ሆኖም ሁለቱ አዘጋጆች “ኦሪጂናሌው ታሪክ የኔ ነው” በሚል ውዝግብ ፈጥረው እንደነበረ አስታውሳለሁ)፡፡
*****
ሃየሎም አርኣያ የተገደለው በየካቲት ወር 1988 ነው፡፡ ታዲያ የርሱ ሞት ከፍተኛ የመነጋገሪያ ርዕስ ሆኖ ነበር፡፡ በኦፊሴል የወጣው የኢትዮጵያ መንግሥት መግለጫ አሟሟቱን ሲያስረዳ “ጄነራል ሃየሎም አርኣያ ጀሚል ያሲን ከሚባል ኤርትራዊ ወጣት ጋር በተፈጠረ ጸብ ተገድሏል” ነው ያለው፡፡ ጥቂት የማይባሉ ሰዎች ግን የሞቱን ምክንያት ሲያስረዱ “ኤርትራ በሓኒሽ ወደቦች ምክንያት ከየመን ጋር በተጣላችበት ወቅት ሃየሎም አርኣያ “ከኤርትራ መንግስት ጋር ያለን ግንኙነት እንደማንኛውም ኢንተርናሽናል ግንኙነት መታየት አለበት፤ በተለይም በወታደራዊ መስክ ያለን ግንኙነት በሀገራችን ላይ አደጋ የሚጋብዝ መሆን የለበትም፤ ከኤርትራ ጎን ሆነን የምንዋጋበት ምክንያት ሊኖር አይገባም” የሚል አቋም በማራመዱ የሻዕቢያ ጥይቶች ሰለባ ለመሆን በቅቷል” ብለው ነበር፡፡ እነዚህ ወገኖች “የሃየሎም አርኣያ ገዳይ ኤርትራዊ መሆንም ይህንኑ ያረጋግጣል” በማለትም አክለዋል፡፡ ከዚህም አልፎ “በስልጣን ላይ የነበረው የአቶ መለስ ዜናዊ አመራር የግድያው ተባባሪ ነው” የሚሉ በርካታ ሰዎች አሉ፡፡
  ሃየሎምን ተኩሶ የገደለው ወጣት ጀሚል ያሲን ከመሞቱ በፊት ከእፎይታ መጽሔት ጋር ባደረገው ቃለ-መጠይቅ “በምሽቱ ሐሺሽ ወስጄ ነበር፤ በሐሺሽ ተገፋፍቼ ነው የገደልኩት እንጂ የተለየ ጠብ ኖሮን አይደለም” የሚል ቃል ነው የተናገረው፡፡ ሃየሎም በሞተበት ወቅት በአጠገቡ የነበሩት ሰዎችም “ወጣት ጀሚል በስካር ጥንብዝ ብሎ ሃየሎምን በባለጌ ስድቦች ይሳደብ ነበር፤ ሃየሎም ለረጅም ጊዜ ከታገሰው በኋላ ትዕግስቱ ሲያልቅበት ሁለት ጥፊ አቀመሰው፣ በዚህ የተናደደው ጀሚል ሽጉጡን ከመኪናው ውስጥ አምጥቶ ገደለው” የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
  መንግሥታት በርካታ ጉዳዮችን ሚስጢራዊ ማድረጋቸው የተለመደ ቢሆንም የሃየሎም ሞት ሙሉ በሙሉ ሚስጢራዊ ሆኖ ቀርቷል ለማለት ምንም ዋስትና የለንም፤ እንዲህ የምንለው ከበርካታ ማዕዘናት በመነሳት ነው፡፡ ለምሳሌ የህወሐት (ኢህአዴግ) ባለስልጣናት በየጊዜው ፓርቲውን ለቀው ይኮበልላሉ፡፡ ሆኖም ከነዚያ ባለስልጣናት መካከል አንዳቸውም ቢሆኑ “ሃየሎም ሻዕቢያ በሸረበው ሴራ ነው የተገደለው” በማለት ሲናገሩ አልሰማናቸውም፡፡ ከአቶ መለስ ጋር ተጋጭተው ከድርጅቱ የወጡትና ከመለስ በላይ ሃየሎምን በቅርበት የሚያውቁት አቶ አረጋዊ በርሀም አቶ መለስን በሃየሎም ግድያ ሲከሷቸው አልተሰሙም፡፡ ከህወሐት ጋር ታሪካዊ ጠላት ሆነው የዘለቁት አቶ አብረሃም ያየህም “ኤርትራ ኢትዮጵያን የወረረችው በአቶ መለስ ዜናዊ አደፋፋሪነት ነው” እያሉ ቢጽፉም ለሃየሎም ሞት ሻዕቢያንም ሆነ አቶ መለስ ዜናዊን ተጠያቂ ሲያደርጉ አላየናቸውም፡፡ ከህወሓት ያፈነገጡት እነ ተወልደ ወልደማሪያምና ስየ አብረሃም ለሻዕቢያ ወረራ በየጊዜው የአቶ መለስን ቡድን ተጠያቂ ማድረጋቸው እንደተጠበቀ ሆኖ የሃየሎምን ግድያ ከኤርትራ ጉዳይ ጋር  ሲያገናኙት አልተደመጡም፡፡
ሻዕቢያ ሃየሎምን አስገድሎት ሊሆን ይችላል የሚሉ ሰዎች በበኩላቸው “ሴራውን ይገልጻሉ” የሚሏቸውን አንዳንድ ምልክቶችን ይደረድራሉ፡፡ ለምሳሌ ሃየሎም ከሞተበት ዕለት ጀምሮ የኤርትራ ሚዲያዎችና ዌብሳይቶች ሰውዬውን በጀግንነቱ ሲያደንቁት እንጂ በአሉታዊ መልኩ ሲያነሱት አይታዩም፡፡ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በሚካሄድበት ወቅት እንኳ የኤርትራ ሬድዮ “የአቶ መለስ አገዛዝ ሃየሎምን የመሰለ የጦር ጀግና ያስበላ የወንበዴ ቡድን ነው” ይል ነበር፡፡ እናም በርካታ ሰዎች “እነዚህ የኤርትራ ሚዲያዎች ሃየሎምን የሚያደንቁት የግድያው ሚስጢር እንዳይወጣ ለማፈን ቢሆንስ?” የሚል የጥርጣሬ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡
 በኛ በኩል “ተጨባጩ እውነታ ይህ ነው” ብለን ምስክርነት መስጠት አንችልም!! በግድያው ዙሪያ በኢንተርኔትም ሆነ በፕሬስ ሲጻፍ የነበረው ሁሉ ጥርጣሬ እንጂ ሐቅ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ጥርጣሬ እውነትም ሊሆን ይችላል፤ ውሸትም ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም የታሪክ ተመራማሪዎች  አንድ ቀን ሐቁን ያሳውቁናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን!! በዚህ አጋጣሚ የማንክደው ነገር ቢኖር ሃየሎም አርኣያ የጦር ሜዳ ጀግና የነበረ መሆኑን ነው፡፡
—-
  አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 7/2007
ገለምሶ-ሀረርጌ


አፈንዲ ሙተቂ
——
ዶ/ር ሃይሌ ፊዳ በፎቶግራፉ ላይ የምትመለከቱት ነው፡፡ ፎቶውን የሰጡን አንጋፋው ደራሲ አበራ ለማ ናቸው፡፡ ጋሼ አበራን እያመሰገንን በሃይሌ ፊዳ አሟሟት ዙሪያ የተጠናቀረውን ይህንን ጽሑፍ ጀባ ብለናችኋል፡፡
                                                                          *****
ኮ/ል መንግሥቱ ሀይለማሪያም “ሀይሌ ፊዳ የተገደለው በገበሬዎች ነው” ባይ ናቸው፡፡ ከጋዜጠኛና ደራሲ ገነት አየለ ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ የሀይሌ ፊዳን ሞት እንዲህ በማለት አስረድተዋል፡፡
ገነት፡ ሀይሌ ፊዳስ? በነሐሴ 1970 ተይዞ ከአንድ ዓመት በኋላ ነገር ከበረደ፤ ሁሉ ነገር ከተረጋጋ በኋላ ነው የተገደለው፡፡ በዚያን ጊዜ የኃይሌ ፊዳ በህይወት መኖር መንግሥትን ያሰጋ ነበር?
መንግሥቱ፡ መቼ ነው የሞተው ሀይሌ ፊዳ?
ገነት፡ በሀምሌ 1971 ነው::
መንግሥቱ፡ ማነው የገደለው?
ገነት፡ እኔ ምን አውቃለሁ? አስከሬኑ ከቀድሞው የራስ አስራተ ካሣ ግቢ ነው ተቆፍሮ የወጣው፡፡ እዚያ ነው የተገኘው፡፡
መንግሥቱ፡ ሀይሌ?
ገነት፡ አዎን! ሀይሌ ፊዳ፡
መንግሥቱ፡ እዚያ ምን ሲሰራ?
ገነት፡ እዚያ ነው አስከሬኑ የተገኘው፡፡
መንግሥቱ፡ እኔ አላውቅም፡፡
ገነት፡ መሞቱንም አያውቁም? እርሱንም እዚህ ከመጡ በኋላ ነው የሰሙት?
መንግሥቱ፡ መኢሶኖች እኮ ጥለውን ሄደዋል፡፡ የሶማሊያ ጥቃት አይሎ ሲመጣ የሻዕቢያዎች ጎራ ስለጠነከረ ከዚህ ከደከመ መንግሥት ጋር ምን እንሰራለን ብለው አይደል እንዴ ጥለው የነጎዱት? በነሱ ሃሳብ እኛ በመዳከማችን ወደፊት ከኛ ጋር በመቀጠል የስልጣን ጥማታቸውን የሚያረኩበት መንገድ ስለማይኖር ልዩ ልዩ ምክንያት ሲያቀርቡ ቆይተው በመጨረሻ ፈርጥጠዋል፡፡ በዚህን ጊዜ እነ መስፍን ካሱ ወደ ሲዳሞ፡ እነ ሀይሌ ፊዳ ወደ ወለጋ ሲሄዱ አግኝቶ ገበሬ ነው የከሰከሳቸው፡፡
ገነት፡ እዚያ ነው የተገደሉት?
መንግሥቱ፡ በሙሉ!
(ገነት አየለ አንበሴ፡ የሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም ትዝታዎች፡ 1984፣ ገጽ 207-208)
                                                                          *****
ሊቀመንበር መንግሥቱ “የሀይሌ ፊዳን መሞት ሰው ነው የነገረኝ” ነው የሚሉት፡፡ ነገር ግን ሀይሌ በነሐሴ 1969 ከተያዘ በኋላ በደርግ ምርመራ ክፍል ሲሰቃይ ቆይቶ እንደተገደለ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ማስረጃ የሆነውንና ሀይሌ ከመሞቱ በፊት የሰጠውን ባለ 36 ገጽ የምርመራ ቃል በልዩ ልዩ መንገዶች ታትሞ አንብበነዋል፡፡ ከሀይሌ ጋር በአንድ ክፍል ታስረው የነበሩ ጓዶችም ሀይሌ በዚያ ወር እንደተገደለ ተናግረዋል፡፡ የደርግ የቅርብ ሰው የነበሩት አቶ ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ) “ነበር” በሚል ርዕስ በጻፉት ባለሁለት ቅጽ መጽሐፍ የምርመራ ቃሉን ከማተማቸውም በላይ ሀይሌ ከሱሉልታ ኬላ ተይዞ ወደ ደርግ ጽ/ቤት በመጣበት ወቅት በብሄራዊ ቤተመንግሥት እንዳዩት መስክረዋል፡፡
    
  በዚህም መሰረት “ሊቀመንበር መንግሥቱ ሀይሌን በእርግጥ ገድለውታል ወይ?” የሚለው ጥያቄ ለአሁኑ ዘመን አይሰራም፡፡ “መንግሥቱ ሀይሌን ለምን ገደሉት?” የሚለው ግን አሁንም ያከራክራል፡፡ ገነት አየለ እንደገለጸችው ሀይሌ በተገደለበት ወቅት ነገሮች ሁሉ በጣም በርደዋል፡፡ የሶማሊያ ወራሪዎች ከምስራቅ ኢትዮጵያ ከተባረሩ አንድ ዓመት አልፎአቸዋል፡፡  ሻዕቢያና ጀብሃ በሁለተኛው አብዮታዊ ሰራዊት ክፉኛ ተደቁሰው ወደ ሱዳንና ወደ ሳሕል በረሃ ገብተዋል፡፡ ከነዚህ ሁለት ክስተቶች ቀደም ብሎም ሀገር ያተራመሰውና ሺዎችን የቀሰፈው የቀይ ሽብር ዘመቻ ደርግ በሚፈልገው መልኩ ተጠናቋል፡፡ አብዮታዊው መንግሥት ከዚያ በፊት ያላየው ሰላምና እርጋታ በሀገሪቱና በሁሉም የስራ መስኮች ሰፍኗል፡፡ ታዲያ በዚህ ሰላማዊ ወቅት ሀይሌ ፊዳን ማስገደሉ ለምን አስፈለገ?
  
  
በርካታ ተመልካቾች የየራሳቸውን ግምት አስቀምጠዋል፡፡ አንዳንዶች ነገሩን ከቂም በቀል ጋር ያያይዙታል፡፡ “መንግሥቱ አንድ ቀን የገላመጠውን እንኳ የማይምር ቂመኛ ነው” -ይላሉ እነዚህ ወገኖች፡፡ የተወሰኑት ደግሞ መንግሥቱ በችሎታና በእውቀት ከርሱ የሚበልጥ ሰው ከታየው ወደፊት ስልጣኔን ይነጥቀኛል በሚል እንደሚያስገድለው ያወሳሉ፡፡ እነዚህኛዎቹ ክርክራቸውን ሲቀጥሉ “መንግሥቱ ሀይለማሪያም ሀይሌ ከእስር ቢለቀቅ ወይም ቢያመልጥ የራሱን ቡድን አደራጅቶ ወይ አንዱን ጄኔራል ተጠግቶ ከስልጣኔ ሊያሽቀነጥረኝ ይችላል” የሚል ፍራቻ ነበረው” ባይ ናቸው፡፡
     
   ከሁለቱ ወገኖች የሚለይ አስተያየት የሚሰጡ ጸሐፊያንና የታሪክ ሰዎችም አሉ፡፡ እነዚህኛዎቹ እንደሚሉት ኮሎኔል መንግሥቱ ሃይለማሪያም በሀይሌ ጉዳይ ላይ የሞት ውሳኔ ያሳለፉት እርሳቸውን ያስደነገጠ አንድ አደገኛ ክስተት ስለተፈጠረ ነው፡፡ እስቲ ታሪኩን አብረን እንየው፡፡
                                                                          *****
     ሊ/ር መንግሥቱ ለጉብኝት ወደ ኩባ ይጋበዛል፡፡ ከጓድ ፊደል ካስትሮ ጋር ጉብኝትና ስብሰባውን ማካሄድ ይጀምራል፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን ለስራ ጉዳይ ወደ ውጪ ሀገር በመሄዱ ህይወቱ ለጥቂት የተረፈችው የመኢሶኑ ዶ/ር ነገደ ጎበዜ አዲስ አበባ መግባቱ ይነገረዋል፡፡ “እንዴት መጣ?” ብሎ ቢጠይቅ “የደቡብ የመንን ፓስፖርት ይዞ፤ ከደቡብ የመን ልዑካን ጋር ተቀላቅሎ” ሆነ መልሱ! (ደቡብ የመን አሁን ከሰሜን ጋር ተዋህዳለች)፡፡ “ዶ/ር ነገደ ተይዟል ወይ?” ብሎ ሲጠይቅ አለመያዙ ተነገረው፡፡ ያለበትን ቦታ ጠይቆ የተሰጠውን መልስ ሲሰማ ደግሞ ሊ/ር መንግሥቱ በድንጋጤ ፈዝዞ ቀረ!
                                                                          *****
 በርግጥ ዶ/ር ነገደ አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ ነገር ግን መጥፎ አጋጣሚ ሆኖ ድሮ ከሚያውቀው የኤርፖርት ደህንነት ሃላፊ ጋር አይን ለአይን ተገጣጠመ፡፡ ደህንነቱ ነገሩን ወዲያኑ ለደርጎች አስታወቀ፡፡ ደርጎችም ነገደ ጎበዜን ለመያዝ ተንቀሳቀሱ፡፡ ሆኖም ዶ/ሩ ኩባ ኤምባሲ ገብቶ ተደበቀ፡፡ ሁኔታው ለጓድ ፊደል ካስትሮ ሲነገራቸው ካስትሮ አማላጅ ሆኑና በነገሩ ውስጥ ገቡ፡፡ በርሳቸው ተማጽኖም ዶ/ር ነገደ ከኤምባሲው ወጥቶ ወደ አውሮጳ ተመለሰ፡፡
  
   ይህ ድርጊት የተከሰተው የሶማሊያ ወረራ ካበቃ ከጥቂት ወራት በኋላ ነበር፡፡ ደርጎች ነገሩን እንደ ኩዴታ ነው የወሰዱት፡፡ ለዚህም ነው በውስጣቸው ከፍተኛ መሸበር የተፈጠረው፡፡ እርግጥ ሀገራቱ ኩዴታ እናድርግ ቢሉ የማስፈጸም አቅሙ ነበራቸው፡፡ በወቅቱ የ”ሶማሊያን ወረራ ለመቀልበስ በተደረገው ዘመቻ አብዮታዊ አጋር ሆኖ የመጣው የኩባ ሀያ ሺ ሜካናይዝድ ጦርና የየመን ሁለት ሺህ መድፈኛ ጦር ኢትዮጵያ ውስጥ ስለነበሩ እነርሱን ይዘው አንድ ነገር ማድረግ ይችሉ ነበር ተብሎ ይገመታል፡፡ የዘመኑ ሀያል ሶሻሊስት ሀገር የሆነችውን ሶቪየት ህብረትንም ለእርዳታ ቢጠሯት “በጄ” ከማለት የምትመለስ አይሆንም-ከመንግሥቱ ይልቅ ኩባና ደቡብ የመን ይበልጡባታልና፡፡ ሆኖም የዶ/ር ነገደን መምጣት ብቻ በማየት “ኩዴታ” ተጠንስሷል ለማለት ይከብዳል፡፡
     ሊ/ር መንግሥቱ በዚህ መረጃ ላይ በመመርኮዝ “ኩዴታ” እንደታቀደባቸው አሰመሩበት፡፡ ሀገራቱ ፈጸሙብኝ ላሉት በደል ደግሞ ቀጥተኛ ምላሽ ከበዳቸው -ምክንያቱም የክፉ ቀን ወዳጆች ናቸውና፡፡ በሌላ በኩል ግን ሊቀመንበሩ ቁጭታቸውን መዋጥ አቃታቸው፡፡    ለምን ቢባል እንኳንስ እንዲህ ዓይነቱን ምልክት አግኝተው ይቅርና በጥርጣሬ ብቻ ብዙዎችን ቀስፈዋልና፡፡ የቀይ ሽብሩ ትርዒት ሳይደመር የተፈጁትን ሰዎች ቤት ይቁጠረው፡፡ ሌ/ኮ/ አጥናፉ አባተን “ለሀገራችን ሶሻሊዝም አይጠቅማትም፤ እንደ ዩጎዝላቪያ የቅይጥ ኢኮኖሚ መርህ መከተል አለብን” በማለታቸው ብቻ አስገድለዋቸዋል፡፡ “ለኤርትራ ጥያቄ ሰላማዊ መፍትሔ ያስፈልጋል” ያሉ በርካታ ጓዶቻቸውን አስረሽነዋል፡፡ አቡነ ቴዎፍሎስ፣ ቄስ ጉዲና ቱምሳ እና ሼኽ ሰይድ ቡደላ (የአብሬት ሼኽ) የመሳሰሉ የሀይማኖት አባቶች ያለ አንዳች ምክንያት ተገድለዋል፡፡ ከዚህ አንጻርም ለዶ/ር ነገደ ጎበዜ ድፍረት የሚሰጡት ቅጣት ከፍተኛ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ግን ዶ/ር ነገደ አልተያዘም፡፡ ስለዚህ ቁጭቱ በምን ይውጣላቸው?
    እንግዲህ በአንዳንዶች እምነት ዶ/ር ሀይሌ ፊዳ የተገደለው በዚህ እርግጠኛነቱ ባልታወቀ የዶ/ር ነገደ ጎበዜ “ኩዴታ” ጦስ ነው፡፡ ኩባና የመንን መበቀል ሲያቅታቸው ቁጭታቸውን በግቢአቸው ባጎሩት እስረኛ ላይ ተወጡት፡፡ ሀይሌን በአንድ ቀዝቃዛ ምሽት አሰናበቱት፡፡
                                                                          *****
     በቅርብ ጊዜ የተገኙ መረጃዎች ግን ከላይ የቀረበውን ታሪክ ዋጋ ቢስ አድርገውታል፡፡ እነዚህ መረጃዎች እንደሚሉት ዶ/ር ነገደ ጎበዜ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው የመጡት በሊቀመንበር መንግሥቱ እውቅና ነው፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ ባሳተሙት መጽሓፋቸው “ነገደ ጎበዜ በመንግሥቱና በኩባዊያን እውቅና መምጣቱን ነግሮኛል” በማለት ጽፈዋል፡፡ ከአሜሪካ የስለላ ምንጮች የተገኘው መረጃም ይህንኑ ያረጋግጣል፡፡ ስለዚህ ደርጎች “መፈንቅለ መንግሥት ሊካሄድ ነበር” እያሉ ወከባ ይፈጥሩ የነበረው ህዝቡንና የተቃዋሚውን ክፍል ለማደናገርና የበለጠ ጸጥ ለማድረግ ነው ማለት ነው፡፡ የሀይሌ ፊዳ ግድያም ከመፈንቅለ መንግሥቱ ጋር አንዳች ግንኙነት አልነበረውም፡፡
  
     በአንጻሩ ደግሞ ሀይሌ ፊዳ የተገደለበት ሀምሌ 1971 በውል ሊመረመር የሚገባው የታሪክ ወቅት ሆኖ ሳለ ምሁራን በጥልቀት ሳያስሱት መቅረታቸው ይገርማል፡፡ ይህ ወር መንግሥቱ ከቀይ ሽብርና ነጭ ሽብር የተረፉ በርካታ ተቃዋሚዎቹን፣ አማካሪዎቹንና ታዋቂ ግለሰቦችን በድብቅ የገደለበት ጊዜ ነበር፡፡ እነ አቡነ ቴዎፍሎስን ጨምሮ የኢህአፓው ብርሀነ መስቀል ረዳ፣ የመኢሶኖቹ ከበደ መንገሻ፣ ንግሥት አዳነ፣ ደስታ ታደሰ፣ መስፍን ካሱ ወዘተ… በዚሁ ጊዜ ነበር የተገደሉት፡፡ “የማዕከል” ጥያቄ ደርጎችን ያናቆረው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡ ኢማሌድህ የሚባለውን የማርክሲስቶች ህብረት ከመሰረቱት አምስት ድርጅቶች (አብዮታዊ ሰደድ፣ መኢሶን፣ ወዝሊግ፣ ኢጭአት እና ማሌሪድ) መካከል መንግሥቱ ከሚመሩት “ሰደድ” ጋር በመድረኩ ላይ የቀረው የማሌሪድ መሪ ተስፋዬ መኮንን የታሰረውና የማሌሪድ ግብአተ ሞትም የተፈጸመውም በዚህ ወር ነበር፡፡ ስለዚህ ያ ታሪካዊ ወቅት የምሁራን እይታ ሊያርፍበት ይገባል፡፡
——
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 21/2006


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——-
   
 አትሳሳቱ! በምስሉ ላይ የምትመለከቱት ሰው ዐረብ አይደለም፡፡ ኢራናዊም አይደለም፡፡ ህንዳዊም አይደለም፡፡ በቀዳሚ ዘመኑ የኢትዮጵያ ፖስፖርት ነበረው፡፡ በኋላ ላይ ግን “ኤርትራ ነጸ መውጣት አለባት” ብሎ ኤርትራዊነትን ሰብኳል፡፡ ለዚህም በረሃ ወርዶ ብረት አንስቷል፡፡ በውጪ መዲናዎች “ሓርነት” እያለ ጮኋል፡፡ ይሁንና ያሰበው ከግቡ ሳይደርስለት ይህቺን ዓለም ተሰናብቷል፡፡ በአንድ ወቅት እርሱ ይመራቸው የነበሩ ወጣቶች ግን ዓላማውን አሳክተዋል፡፡
                                                                          *****
     “ጀብሃ” እና “ሻዕቢያ” በሚል ርዕስ የቀረበውን ተከታታይ ጽሑፍ ተከታትላችኋልን? እንዲያ ከሆነ “ሻዕቢያ” የተሰኘው ድርጅት ከጀብሃ ተገንጥሎ በሁለት እግሩ እንዲቆም የረዳው አንድ አደገኛ “ዲፕሎማት” እንደሆነ ተረድታችኋል ማለት ነው፡፡ ያ “ዲፕሎማት” በምስሉ ላይ የምትመለከቱት ሰው ነው፡፡ የዚህ ሰው ልደት የተበሰረው በሞቃት አየሯ በምትታወቀው ውቢቷ የምጽዋ ከተማ አጠገብ ባለችው “ሀርጊጎ” በተሰኘች ባህረ-ገብ መንደር ነው፡፡ ወላጆቹ በምሥራቅ ኤርትራ ከሚኖሩት የአሳውርታ (ሳሆ) ብሄረሰብ ነው የተገኙት:: የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በምጽዋ ካገባደደ በኋላ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአዲስ አበባ ከተማ አጠናቋል፡፡ በ1950ዎቹ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ በመምህርነት ተመርቋል፡፡ በስራው ዓለም ወደ ምጽዋ ከተማ ተመልሶ በትምህርት ቤት ዳይሬክተርነት አገልግሏል፡፡ በዚህ ሙያ ላይ እያለም ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትቀላቀል ሲደረግ እርምጃውን የተቃወመው “ማህበር ሸውአተ” (ሀረካ) አባል ሆኗል፡፡ በ1961 “ተጋድሎ ሐርነት ኤርትራ” (ጀብሐ) ሲመሰረት ደግሞ ከሀረካ ወጥቶ ጀብሃን ተቀላቅሏል፡፡ ድርጅቱንም ለረጅም ጊዜ በውጪ ጉዳይ ኃላፊነት አገልግሏል፡፡ ድርጅቱ እስከ አሁን ድረስ የሚታወቅበትን “ሰውራ” የተሰኘ መጽሔት መስርቷል፡፡ ከ1970 በኋላ ግን የድርጅቱን አካሄድ በመቃወም “ህዝባዊ ሀይሊ” የተሰኘ ንቅናቄ ጀምሯል፡፡ ይህንን ቡድን “ሰልፊ ነጻነት” ከተሰኘው የደገኛ ኤርትራዊያን ቡድን ጋር በማዋሃድ በታሪክ ገጾች “ህዝባዊ ሓርነት ሀይልታት” ወይንም “ሻዕቢያ” የተሰኘውን ጥምረት መስርቷል፡፡ ጥምረቱንም እንደ “ውስጠ ዘ” (defacto) ሊቀመንበር እና እንደ ውጪ ጉዳይ ሃላፊ ሆኖ አገልግሏል፡፡ በስተመጨረሻው ግን ከወጣቶቹ ጋር መግባባት ስላልቻለ በልዩነት ተሰናብቷል፡፡
     ይህ ሰው እ.ኤ.አ. በ1978 ከጀብሃ ጋር በጋራ አብሮ የመስራት ስምምነት የተፈራረመ ሲሆን በ1980 ገደማም የርሱን መስመር ከሚከተሉ ሌሎች ታጋዮች ጋር “ህዝባዊ ሓርነት ሀይልታት ሰውራዊ ባይቶ” የተሰኘ ድርጅት መስርቶ ነበር፡፡ ሆኖም በወቅቱ “ሻዕቢያ” የተሰኘው ግንባር ከርሱ ጋር በሀሳብ የተለዩትን ድርጅቶች እያሳደደ ይመታ ስለነበር ወደ ሀገር ቤት ገብቶ የትጥቅ ትግል ለመጀመር አልቻለም፡፡ ቢሆንም ሰውዬው በፖለቲካው መስክ አልሰነፈም፡፡ በውጪው ዓለም ከፍተኛ የዲፕሎማሲ ትግል ማድረጉን ቀጥሏል፡፡ በ1987 ግን ይህችን ዓለም ተሰናብቷል፡፡
                                                                          *****
  ሰውየውን አውቃችሁታል አይደል? አዎን! ዑስማን ሳልህ ሳቤ ነው፡፡ ዛሬ በኢሳያስ የሚመራውን ህዝባዊ ግንባር (ሻዕቢያ) የመሰረተው እርሱ ነው፡፡ ይህ ሰው በታሪክ ምሁራን እጅግ ከፍተኛ ችሎታ ያለው ፖለቲከኛ ተብሎ ነው የሚጠቀሰው፡፡ በርካታ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ድርጅቶች በጨቅላነታቸው ዘመን የርሱ እርዳታ በእጅጉ አስፈልጎአቸዋል፡፡ የኢህአፓ ታጋዮች የትጥቅ ትግል እንዲጀምሩ ያበቃቸውን ስልጠና ያገኙት በርሱ አማካኝነት ነው፡፡ ከአስር የማያንሱ ጠመንዣዎችንም ያስገኘላቸው እርሱ ነው፡፡ የኦነግ ጠንሳሾች የሚባሉት እነ ጃራ አባገዳ በመሳሪያ ተደራጅተው ትግሉን ለመጀመር የበቁት እርሱ ባደረገላቸው እርዳታ ታግዘው ነው፡፡ ለሌሎችም እንዲሁ የእርዳታ እጁን ዘርግቷል፡፡
  “ሻዕቢያዎች” ከዑስማን ሳልህ ሳቤ ጋር መጣላታቸው እሙን ነው፡፡ በአንድ ዘመን ሀይለኛ የፕሮፓጋንዳ ጦርነት አካሂደውበታል፡፡ ከነጻነት በኋላ ግን በትግሉ ላበረከተው አስተዋጽኦ እውቅና ሰጥተዋል፡፡ በርሱ ስም ትምህርት ቤትና ጎዳና ሰይመዋል፡፡ ይህም ከጀብሃ ጋር ንክኪ የነበረው ማንኛውም ግለሰብ ያላገኘው እድል ነው፡፡ ከርሱ ጋር ይህንን እድል በጥቂቱ ለመጋራት የቻለው አንጋፋው የጀብሃ ታጋይ ኢድሪስ ገላውዴዎስ ብቻ ነው፡፡
 —–
አፈንዲ ሙተቂ
ታሕሳስ 1/2006


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——-
አንዳንዶች “ነቢዩ ሙሐመድን (ሰ.ዐ.ወ) ትጠላላችሁ፤ በነቢዩ ላይ ሰለዋት አታወርዱም” ይሉናል፡፡ ሐቁ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ በነቢዩ ላይ ሰላምና ሰለዋት በማውረድ ከኛ የሚቀድም ማን ነው? እንዲያውም የነቢዩን ታላቅ ደረጃ በዜማ እየዘከርን እና ገድላቸውን እየተረክን ነው በርሳቸው ላይ ሰላምና ሰለዋት የምናወርደው:: ይህንን እውነታ ያስረዳልን ዘንድ የሱፊ ሼኾቻችን ትተውልን ያለፉትን አንድ “ነሺዳ” (የነቢዩ ውዳሴ”) እንጋብዛችሁ፡፡
  *****  *****  *****
    ነሺዳው መጠሪያ “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ይሰኛል፡፡ “አሕመድ ወዳጄ ሆይ” እንደማለት ነው፡፡ እኛ ስናሰፋው “ አሕመድ የልቤ ወዳጅ”፤ “አሕመድ የነፍሴ ስር” ልንለው እንችላለን፡ (“አሕመድ” የነቢዩ ሙሐመድ -ሰ.ዐ.ወ- ሁለተኛ ስም ነው፡፡ ነቢዩ በመጨረሻው ቀን/የውመል ቂያማ የሚጠሩት አሕመድ በተሰኘው ስማቸው ነው)፡፡
    
   ይህንን “ነሺዳ” ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት በ1995 ዓ.ል. ይመስለኛል፡፡ ነሺዳውን በህብረት ሲዘምሩ የነበሩት መሰረቱን በኦምዱርማን ከተማ ባደረገውና “ፊርቀቱ-ሳሕዋ” በሚባለው ዝነኛ የሱዳን የነሺዳ ቡድን የታቀፉት ስድስት ወጣቶች ነበሩ፡፡ የቡድኑ አባላት የሚያዜሙት በአብዛኛው በታዋቂው ሼኽ ዐብዱረሒም አል-ቡረኢ የተጻፉትንና “መዲሕ” የሚባሉትን የነቢዩን ግጥማዊ መወድሶች በመሆኑ “አሕመድ ያ ሐቢቢ”ም የሼኽ አል-ቡረኢ ድርሰት ይመስለኝ ነበር፡፡ በ2001 ወደ ሀረር ከመጣሁ ወዲህ ግን “አሕመድ ያ ሐቢቢ” በአንድ ዘመንና በአንድ ስፍራ ያልተገደበ ውዳሴ እንደሆነ ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ለዚህ ያበቃኝ ደግሞ በቀድሞ ዘመናት የተጻፈ አንድ “የመዲህ” ኪታብ (መጽሐፍ) በሀረር ለማየት መታደሌ ነው፡፡
     በርግጥም “የፊርቀቱ ሳሕዋ” ወጣቶች የሚዘምሩት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” እና ከሀረር ያገኘሁት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” አንድ መሰረት ያላቸው መሆኑን ከግጥሞቹ አሰካክ ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሆኖም በመካከላቸው መጠነኛ ልዩነቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ ሱዳናዊያኑ ወጣቶች “አሕመድ ያ ሐቢቢ” በሚል ሐረግ የሚጀምረውን ባለሁለት መስመር ግጥም እንደ አዝማች አድርገው ይደጋግሙታል፡፡ የሀረሩ “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ግን አዝማች የለውም፤ በዚህኛው ስልት “አሕመድ ያ ሐቢቢ” የሚለው ሐረግ አንድ ጊዜ ከታየ በኋላ አይደገምም፡፡ በሁለተኛ ደረጃም ሁለቱ የ“አሕመድ ያ ሐቢቢ” ስልቶች በግጥሞቻቸው ብዛት ይለያያሉ፡፡ የሀረሩ ስልት በኦምዱርማኑ ስልት ውስጥ የሌሉ ግጥሞቹ አሉት፡፡ በመሆኑም በግጥሞቹ ብዛት ከኦምዱርማኑ ስልት ይበልጣል፡፡
  
   የሀረሩ ስልት በትርፍነት ከያዛቸው ግጥሞች ውጪ ባሉት ግጥሞቹ ከኦምዱርማኑ ስልት ጋር የመመሳሰል ነገር ይታይበታል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን በሁለቱ ስልቶች ያሉት ግጥሞች መቶ በመቶ የሚመሳሰሉበት ሁኔታ የለም፡፡ ግጥሞቹ አንዳንዴ በሁለት ስንኞቻቸው ብቻ ይመሳሰሉና በሶስተኛው ስንኝ ይለያያሉ፡፡ ሲያሻቸው ደግሞ በተመሳሳይ ሁኔታ እየተጓዙ በቃላት ደረጃ ይለያያሉ፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ሁሉም ስንኞች እኩል ርዝመት ነው ያላቸው፡፡ ሁላቸውም “ሰላም ዓለይከ” በሚል ሐረግ የሚጀምሩ መሆናቸው ደግሞ የነሺዳው ኪናዊ ውበት ምንጭ ሆኗል፡፡
 
   በዚህ መጣጥፍ የምጋብዛችሁ የኦምዱርማኑን “አሕመድ ያ ሐቢቢ” ነው፡፡ ከኔ ጋር ነሺዳውን በ“ፊርቀቱ ሳሕዋ” ዜማ ለመዘመር ተዘጋጁ! ዳይ!!!
(ዐረብኛውን ወደ አማርኛ መተርጎም ይከብዳል፡፡ ስለዚህ እንዳለ ልተተው ተገድጃለሁ)፡፡
  *****  *****  *****
አሕመድ ያ ሐቢቢ ሰላም ዓለይከ
ያ ሚስኪ ወጢቢ ሰላም ዓለይከ
ሰላም ዓለይከ ዜይነል አንቢያኢ
ሰላም ዓሌይከ አትቀል አትቂያኢ
ሰላም ዓለይከ አስፉል አስፊያኢ
ሰላም አለይከ ሚን ረብቢ-ሰማኢ
ሰላም ዓለይከ ዳኢመን ቢላ ኢንቲሃኢ
ሰላም ዓለይከ
—-
ሰላም ዐለል ሙቀደም ሊል ኢማማ
ሰላም ዐለል ሙዘለል ቢል ጘማማ
ሰላም ዐለል ሙዘወጅ ሊል ከራማ
ሰላም ዐለል ሙሰቢህ ሊል ሰላማ
ሰላም ዐለል ኹላሳ ሚን ቱሐማ
ሰላም ዐለል ሙሸፍፊዕ ቢልቂያማ
ሰላም ዓለይከ
—–
ሰላም ዐለይከ ጣሃ ያ ሐቢቢ
ሰላም ዐለይከ ያ ሚስኪ ወጢቢ
ሰላም ዐለይከ ያ -ማሂ ዙኑቢ
ሰላም ዐለይከ ያ ጃሊል ኩሩቢ
ሰላም ዓለይከ
 —–
ሰላም ዐለይከ ያ ኸይረል አናሚ
ሰላም ዐለይከ ያ በድረ ተማሚ
ሰላም ዐለይከ ያ ኑረል ዘላሚ
ሰላም ዐለይከ ያ ኩለል ጉራም
ሰላም ዐለይከ
—-
ሰላም ዐለይከ ያ ዘል ሙእጂዛቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ዘል በይናቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ሐቢቡ ዛቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ሐሱነ-ስ-ሲፋቲ
ሰላም ዐለይከ ያ ዙኽረል ዑሳቲ
ሰላም ዐለይከ
—-
ሰላም ዐለይከ አሕመድ ያ ሙሐመድ
ሰላም ዐለይከ ያ ጣሃ ያ ሙመጀድ
ሰላም ዐለይከ ዘል መንተፈረጅ
ሰላም ዐለይከ
ሰላም ዐለይከ ያ ሩክነ-ሰላሂ
ሰላም ዐለይከ ያ ዘይነል ኢላሂ
ሰላም ዐለይከ ያ ዳኢል ፈላሒ
ሰላም ዐለይከ
አሕመድ ያ ሐቢቢ ሰላም ዓለይከ
ያ ሚስኪ ወጢቢ ሰላም ዓለይከ
  *****  *****  *****
አፈንዲ ሙተቂ
ሸገር- አዲስ አበባ
ጥቅምት 2/2006



ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——
  ይህ ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ነው፡፡ ኢህአፓዎች ከማንም በላይ የሚያከብሩትና የሚያደንቁት አርበኛና የለውጥ ብስራት ነጋሪ ፋኖ! የጽናትና የቆራጥነት ተምሳሌት ሆኖ በየዓመቱ የሚዘከር የዚያ ትውልድ ታላቅ ሰው!

       በእርግጥም ተስፋዬ ደበሳይ ቆራጥ ነበር፡፡ ላመነበት ዓላማ ሺዎችን አንቀሳቅሷል፡፡ ለጠላቶቹ ሳይንበረከክ ህይወቱን ሰውቷል፡፡ በርሱ ሞት ያዘኑት ኢህአፓዎች “ተስፋዬን ከምናጣ ሌሎች የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቶቻችን በሙሉ ቢጠፉ ይሻለን ነበር” በማለት መሪር ሐዘናቸውን አሰምተዋል፡፡ የደርግ መንግሥት እርሱ በሞተበት ዕለት ባወጣው መግለጫ አንድ ክፍለ ጦር ሰራዊት የተደመሰሰ ያህል ነበር የፎከረው፡፡
    ተስፋዬ ደበሳይ ማን ነው? በኢህአፓ ውስጥ የነበረው ሚና ምን ይመስል ነበር?… ህይወቱ የተፈጸመው እንዴት ነው? እስቲ በጥቂቱ እንየው፡፡
                                                                          *****
    ኢሮብ በትግራይ ክፍለ ሀገር፣ አጋሜ አውራጃ ውስጥ የምትገኝ ወረዳ ናት (በአሁኑ የአስተዳደር አወቃቀር በትግራይ ክልል፣ ምስራቃዊ ዞን ውስጥ ነው የምትገኘው)፡፡ በዚህች ወረዳ ከትግርኛ ተናጋሪው ብሄረ-ትግራይ በተጨማሪ ኢሮብ የሚባለው አነስተኛ ብሄረሰብ ይኖራል፡፡ ይህ ህዝብ በውስጡ ሶስት ዐይነት ማህበረሰቦች አሉት፡፡ አንደኛው ደመክኒቶ ይባላል፡፡ የዚህ ማህበረሰብ አባላት የካቶሊክ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ሁለተኛው ማህበረሰብ “ሀሳበላ” የሚባል ሲሆን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች ይበዙበታል፡፡ ሶስተኛው ማህበረሰብ “ዳልገዳ” ይባላል፡፡ እነዚህኛዎቹ ደግሞ ሙስሊሞች ናቸው፡፡ እነዚህ ማህበረሰቦች የሚናገሩት ቋንቋ በኤርትራ ምድር ከሚነገረው የሳሆ ቋንቋ ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ ሆኖም ኢሮብ እና ሳሆ በኢኮኖሚ ስምሪታቸው ይለያያሉ፡፡ የሳሆ ህዝብ ሙሉ በሙሉ አርብቶ አደር ነው፡፡ ኢሮቦች ግን በእርሻ ስራና በአነስተኛ ዕደ-ጥበባት ነው የሚተዳደሩት፡፡ የኢሮብ ወረዳ ተራራና ሸንተረር ይበዛዋል፡፡ በአካባቢው ካሉት ተራሮች መካከል “አሲምባ” እና “አይጋ” ትልልቆቹ ናቸው፡፡ 
    
   በዚህች የኢሮብ ወረዳ ውስጥ አሊቴና የምትባል አነስተኛ መንደር አለች፡፡ ይህች መንደር የአጋሜ አውራጃ ርዕሰ ከተማ ከሆነችው አዲግራት 35 ኪሎ ሜትር ያህል ትርቃለች፡፡ የመንደሪቷ ነዋሪዎች በአብዛኛው ካቶሊክ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ተሰፋዬ ደበሳይ በዚያች አነስተኛ መንደር ውስጥ ነው በ1933 የተወለደው፡፡ ወላጅ አባቱ አቶ ደበሳይ ካህሳይ ይባላሉ፡፡ እናቱ ደግሞ ወ/ሮ ምህረታ ዓዶ-ዑማር ነበሩ፡፡ ተስፋዬ የቤተሰቡ የበኩር እና ብቸኛ ወንድ ልጅ ነው፡፡ ከርሱ በኋላ የተወለዱት ስድስት ልጆች በሙሉ ሴቶች ናቸው (ለዚህ ጽሑፍ የመረጃ ምንጭ ከሆነው የመጋቢት ወር/2005 የኢህአፓ ዘገባ ለመረዳት እንደተቻለው ከስድስት እህቶቹ መካከል አምስቱ በህይወት ይገኛሉ፤ ወላጅ አባቱም በህይወት አሉ)፡፡
  
     አሊቴና በዚያ ዘመን ትምህርት ቤት አልነበራትም፡፡ ስለዚህ ህጻኑ ተስፋዬ የትምህርት ጉጉት ቢኖረውም እድሜው አስር ዓመት እስኪሆነው ድረስ ትምህርት ቤት ለመግባት አልታደለም፡፡ በ1943 ግን አዲግራት ከሚኖሩት አክስቱ ዘንድ ሄደና ትምህርት ቤት እንዲያስገቡት ለመናቸው፡፡ አክስቱም በከተማዋ ከሚገኝ ታዋቂ የካቶሊክ ሚሽን ትምህርት ቤት አስገቡት፡፡ ተስፋዬም እስከ ስምንተኛ ክፍል በዚሁ ት/ቤት ከተማረ በኋላ ዘጠኛ ክፍልን መቀሌ በሚገኘው አጼ ዮሐንስ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት አጠናቀቀ፡፡ ይሁንና በወቅቱ የትምህርት ወጪውን በራሱ ሸፍኖ መማር እንደማይችል በመረዳቱ ፊት ወደ ነበረበት የካቶሊክ ት/ቤት ተመለሰ፡፡ እዚያም እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል ከተማረ በኋላ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ጣሊያን ሀገር ተላከ፡፡ በሀገረ ኢጣሊያ ሮም ከተማ ካለው Urbaniana University በፍልስፍና ትምህርት የዶክትሬት ዲግሪውን ተቀበለ፡፡
    ተስፋዬ በስራው ዓለም ሲሰማራ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰራበት መስሪያ ቤት የማስታወቂያና መርሐ ብሄር ሚኒስቴር ነበር፡፡ በዚህ መስሪያ ቤት የምርምር ክፍል ሃላፊ ሆኖ እየሰራ በማታው ክፍል የአባዲና ፖሊስ ኮሌጅ አስተማሪ ለመሆን በቅቷል፡፡ በ1964 ለተጨማሪ ስልጠና ወደ አውሮጳ (ስዊዘርላንድ) ተልኳል፡፡ በዚያ እያለም በመቀጣጠል ላይ የነበረው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ልቡን ስለወሰደው ትምህርቱን ትቶ ሙሉ በሙሉ ወደዚያው ገብቷል፡፡
   
     ታዲያ እርሱ ወደ ስዊዘርላንድ በሄደበት ወቅት በአውሮጳው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማህበር እና በአሜሪካው የተማሪዎች ማህበር መካከል ከፍተኛ ውዝግብ ይካሄድ ነበር፡፡ ሁለቱ ማህበሮች የተወዛገቡት የድርጅት ምስረታና አደረጃጀት፣ የኤርትራ ጥያቄ፣ የብሄረሰቦች መብት፣ የትጥቅ ትግል አስፈላጊነት በመሳሰሉ አርዕስተ ነገሮች ዙሪያ ነበር፡፡ በጊዜው የድርጅት አስኳል ለመመስረት ጥረት ያደርግ የነበረው የአልጄሪያው የስደተኛ ተማሪዎች ቡድን ከአሜሪካው ማህበር ጋር ተቀራራቢ አቋም አሳየ፡፡ የአውሮጳው ማህበር መሪዎች በሀገር ቤት ከነበሩ ጥቂት ተማሪዎች ጋር አንድ ዓይነት አቋም ላይ ደረሱ፡፡ ተስፋዬ ደበሳይ ግን የአውሮጳው ማህበር መሪዎችን ውሳኔ በመቃወም ከአልጄሪያው ቡድን ጋር ወገነ፡፡ በዚህም መሰረት የአልጄሪያው ቡድን፣ የአሜሪካው ቡድንና አውሮጳ የነበሩት ጥቂት ተማሪዎች በድርጅት ምስረታ ሂደት ላይ መነጋገር ጀመሩ፡፡ ውይይቱ ለወራት ሲብላላ ከቆየ በኋላ በዓለም ዙሪያ ተበታትነው የነበሩ ሌሎች ኢትዮጵያዊ ተማሪዎችንም ማካለል ጀመረ፡፡ በስተመጨረሻም በሚያዚያ ወር 1964 “የኢትዮጵያ ህዝቦች አርነት ድርጅት” (ኢህአድ) ተወለደ፡፡ ተስፋዬ ደበሳይም ለድርጅቱ አመራር ከተመረጡ ሰባት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት አንዱ ሆነ፡፡
                                                                          *****
       ኢህአድ የተወለደው በውጪ ሀገር ነው፡፡ ከ1964-1966 በነበሩት ዓመታት ዋነኛ ስራው ድርጅቱን ማስተዋወቅና አባላትን ማሰባሰብ ነበር፡፡ ከፍልስጥኤም ነጻ አውጪ ድርጅትና ከኤርትራ ግንባሮች የተሰጠውን ድጋፍ በመጠቀም የትጥቅ ትግል የመጀመር እንቅስቃሴ ሲያደርግም ቆይቷል፡፡ የድርጅቱ ቀዳሚ ዓላማ ከገጠር በሚጀመር የትጥቅ ትግል በረጅም ጊዜ የስርዓት ለውጥ ማምጣት ነበር፡፡ የኢህአድ መሪዎችም ድርጅቱ ቀዳሚ ሰራዊቱን ሊያሰማራበት ወዳሰበው የአሲምባ ተራራ በመሄድ ወታደራዊና ፖለቲካዊ አመራር እንዲሰጡ ለማድረግ ታስቧል፡፡ ይሁንና በ1966 የፈነዳው የኢትዮጵያ አብዮት የትግሉን አቅጣጫ ሙሉ በሙሉ ቀየረው፡፡ የአሮጌው ስርዓት መውደቅ አይቀሬ እንደሆነ ሁሉም በየፊናው አወቀ፡፡ “በርሱ ቦታ ተተክቶ ሀገሪቱን የሚመራው ማን ነው?” የሚለው ጥያቄ ግን አነጋጋሪ ሆነ፡፡ በዚህም በተራማጅ አብዮተኞች መካከል ከፍተኛ ውይይት ተቀሰቀሰ፡፡ በመደምደሚያውም የፓርቲ ቅርጽ የነበራቸው ቡድኖች በከተሞች አካባቢ የፖለቲካ ትግል ቢያደርጉ ጠቀሜታው ከፍ ያለ እንደሚሆን ከስምምነት ላይ ተደረሰ፡፡ በመሆኑም በውጪ ሀገር የነበረው የኢህአድ አመራር ወደ ሀገሪቷ ለመግባት ወሰነ፡፡
   
     ከኢህአድ ከፍተኛ መሪዎች መካከል በቅድሚያ ወደ አዲስ አበባ የገባው ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ነው፡፡ ጊዜውም ሰኔ 1966 ነበር፡፡ በወቅቱ የወታደሮች ቡድን የሆነው ደርግ ተመስርቶ የአጼውን መንግሥት ለመጣል እያኮበኮበ ነበር፡፡ በሀምሌ ወር አጋማሽ ላይ ደርግ የልጅ እንዳልካቸውን ካቢኔ በመሻር ልጅ ሚካኤል እምሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲሆኑ መረጣቸው፡፡ ልጅ ሚካኤልም ካቢኔአቸውን ሲያቋቁሙ በስዊዘርላንድ የሚያውቁትን ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይን የመሬት ይዞታ ሚኒስትር እንዲሆን ጠየቁት፡፡ እርሱ ግን ከውጪ የመጣው ለዚያ አልነበረምና አንዳች ምክንያት ፈጥሮ አሉታዊ መልስ ሰጣቸው፡፡ በምትኩ በመስሪያ ቤቱ በኤክስፐርትነት ቢቀጠር ለመስራት ፈቃደኛ እንደሆነ ገለጸላቸው፡፡ በዚህም መሰረት ከነሐሴ 1966 ጀምሮ የመስሪያ ቤቱ ሰራተኛ ሆነ፡፡
 
   ተስፋዬ ወደ ሀገር ቤት ከተመለሰ በኋላ ድርጅቱን በማስፋፋትና አባላትን በማደራጀት ስራ ላይ ነበር የተጠመደው፡፡ የድርጅቱ ልሳን የሆነችውን “ዲሞክራሲያ” ጋዜጣን ከሚያወጡ አርታኢያን መካከልም አንዱ ነበር፡፡ በድርጅቱ የመጀመሪያ ጉባኤ ዋና ጸሐፊ ሆኖ የተመረጠው ብርሃነ መስቀል ረዳ ከሰራዊቱ ጋር ስለነበር በርሱ ቦታ በጊዜያዊነት አመራር የሚሰጠውም ተስፋዬ ደበሳይ ነበር፡፡  በወቅቱ በድርጅቱ አመራር ላይ ከነበሩትም መካከል በዕድሜም ሆነ በትምህርት ደረጃ የሚበልጠው እርሱ ነበር፡፡
   
   ተስፋዬ እስከ ታህሳስ 1967 በአዲስ አበባ ከተማ ከቆየ በኋላ ከመሬት ይዞታ ጋር ለተያያዘ የመስክ ስራ ወደ ትግራይ ተጓዘ፡፡ እግረ መንገዱንም አሲምባ የሚገኘውን የድርጅቱን ጀማሪ ሰራዊት ለመጎብኘት ወደዚያው ጎራ አለ፡፡ በጊዜው የነበረውን የሀገሪቱን የፖለቲካ ሁኔታ ለሰራዊቱ ካብራራ በኋላ ግን ያልተጠበቀ ችግር ተከሰተ፡፡ ስምንት ያህል የሰራዊቱ አባላት ከጀማሪ ሰራዊቱ በመነጠል ለደርግ እጃቸውን ሰጡ (እጃቸውን የሰጡት ሰዎች ተስፋዬ መኮንን፣ ኃይለ እየሱስ ወልደ ሰንበት፣ አበበ በየነ፣ ዘከሪያ መሐመድ፣ አያሌው ከበደ፣ ጋሻው መንግሥቱ፣ ሀይሌ ወልደ ጊዮርጊስና ዳዊት አሰፋ ነበሩ፤ እነዚህ ሰዎች በ1968 መጀመሪያ ላይ “ማሌሪድ”፣ ማለትም “የማርክሲስት ሌኒኒስት ሪቮሉሽናሪ ድርጅት”ን መስርተዋል)፡፡ ታዲያ የነዚህ ሰዎች ከኢህአፓ አፈንግጦ መውጣት የዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይን ማንነት አጋለጠው፡፡ በመሆኑም ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ህቡዕ ለመግባት ተገደደ፡፡
                                                                          *****
   ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ህቡዕ ከገባ በኋላ የሙሉ ጊዜ አብዮታዊ ሆኗል፡፡ ኢህአድን በሙሉ አቅሙ አገልግሏል፡፡ በነሃሴ ወር 1967 ድርጅቱ ስሙን ቀይሮ “ኢህአፓ” (የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ) የተሰኘውን ዝነኛ መጠሪያውን የያዘበትን ጉባኤ በዋናነት ያዘጋጀውም እርሱ ነው፡፡ የድርጅቱ የፍልስፍና ሊቅ (ideologue) ሆኖ የሚያገለግለውም እርሱ ነበር፡፡ በኢህአፓ መስራች ጉባኤ “ዋና ጸሐፊ” የሚባል የስልጣን ተዋረድ ሲሻር በቀዳሚነት የማዕከላዊ ኮሚቴ ጸሐፊ ሆኖ ማገልገል የጀመረው እርሱ ነበር (ይህ የጸሐፊነት ቦታ በየጊዜው ይለዋወጥ ነበር፤ ጸሐፊው የሚመረጠውም በፓርቲው ጉባኤ ሳይሆን በፖሊት ቢሮው ነው)፡፡
   እስከ 1968 አጋማሽ ድረስ በነበረው ጊዜ የኢህአፓ አመራሮች ማንነት በግልጽ አይታወቅም፡፡ በዚያን ጊዜ ህቡዕ ለመግባት የተገደዱት ብርሃነ መስቀል ረዳ እና ተስፋዬ ደበሳይ ብቻ ናቸው፡፡ በመሆኑም አብዛኛው የፓርቲው ስራ የሚከወነው በተስፋዬ ነበር (ብርሃነ መስቀል ለፖሊት ቢሮው ስላልተመረጠ ከፍተኛ ሃላፊነት አልተሰጠውም፤ በተጨማሪም ከሌሎች መሪዎች ጋር መነታረክ ጀምሮ ነበር) ፡፡
   
    የህዝብ ድርጅት ጉዳይ ጊዜያዊ ጽ/ቤት ከተመሰረተ በኋላ ግን አመራሩን ለአደጋ የሚያጋልጥ ሁኔታ ተከሰተ፡፡ በጽ/ቤቱ የተመረጡት ከፍተኛ ካድሬዎች የኢህአፓ መሪዎችን ስለሚያውቋቸው ለደርግ አሳልፈው ይሰጡአቸዋል የሚል ስጋት ሰፈነ፡፡ በመሆኑም በ1968 መጨረሻ ገደማ ሁሉም መሪዎች ህቡዕ ለመግባት ተገደዱ፡፡ ታዲያ የኢህአፓ የትግል ስትራቴጂም መለወጥ የጀመረው ከዚህ ወቅት ጀምሮ ነው፡፡ ከ1968 ክረምት ወራት በፊት በከተሞች አካባቢ የፖለቲካ ትግል ብቻ ያደርግ የነበረው ኢህአፓ የደርግ ፋሺስትነትን ለመከላከል በሚል የከተማ ትጥቅ ትግል የጀመረው ያኔ ነው፡፡
      አንዳንድ ወገኖች የትጥቅ ትግሉ በዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ግፊት የመጣ ነው ይላሉ፡፡ ከሊቀመንበር መንግሥቱ ኃይለማሪያም ጀምሮ መገደል ያለባቸውን ከፍተኛ የደርግና የመኢሶን ባለስልጣናት ዝርዝር እያዘጋጀ የሞት ፍርድ ያስወስን የነበረው ተስፋዬ ደበሳይ ነው በማለት ይሞግታሉ፡፡ ከዚህ እልፍ ሲል ደግሞ የተስፋዬን ትግሬነት በመጥቀስ ብቻ ሻዕቢያ በአዲስ አበባ ከተማ ሽብር ለመቀስቀስ የመደበው የጥፋት ወኪል ነው የሚል መረጃ የሚያስነብቡ ጽሁፎችን ማየት የተለመደ ሆኗል (ለነገሩ ተስፋዬ የኢሮብ ተወላጅ ነው እንጂ ትግሬ አልነበረም)፡፡ ይሁንና እንዲህ ዓይነቱን የተናጥል ክስ በተስፋዬ ላይ የሚያጠናክር ማስረጃ የለም፡፡ ኢህአፓ የከተማ ትጥቅ ትግል እንዲጀምር የወሰኑት ብዙሃኑ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ናቸው እንጂ ተስፋዬ ደበሳይ ብቻ አልነበረም፤ ውሳኔውን የተቃወሙት ጌታቸው ማሩ እና ብርሃነ መስቀል ረዳ ብቻ ነበሩ (በጊዜው የኢህአፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት የነበሩት ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ፣ ዮሐንስ ብርሃኔ፣ ዮሴፍ አዳነ፣ ክፍሉ ታደሰ፣ ክፍሉ ተፈራ፣ ዘርዑ ክህሸን፣ ኢያሱ አለማየሁ፣ ሳሙኤል አለማየሁ፣ አበራ ዋቅጅራ፣ ፍቅሬ ዘርጋው፣ ጸጋዬ ገብረመድህን፣ ብርሃነ መስቀል ረዳ፣ ጌታቸው ማሩ እና ጸሎተ ህዝቅያስ ነበሩ)፡፡
                                                                          *****
  መስከረም 13 ቀን 1969፡፡ በዚህች ዕለት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያምን ለመግደል ያልተሳካ ሙከራ ተደረገ፡፡ በዚህም የተነሳ ኮሎኔሉ ኢህአፓን ለማጥፋት ቆርጠው ተነሱ፡፡ በስውር የሚያካሄዱትን ርሸና ይፋ ማውጣት ጀመሩ፡፡ በታህሳስ ወር የኮሎኔሉን እርምጃ የሚቃወሙ መኮንኖች በደርግ ውስጥ መዋቅራዊ ለውጥ አካሄዱ፡፡ ይሁን እንጂ ከአንድ ወር በኋላ (ጥር 25/1969) ኮሎኔል መንግስቱ ማንም ባላሰበው መንገድ ጠላቶቻቸውን በማጥፋት “ለምሳሌ ያሰቡንን ቁርስ አደረግናቸው” በማለት አወጁ፡፡ “አብዮቱ ከተከላካይነት ወደ አጥቂነት ተሸጋግሯል” ተባለ፡፡ “ቀይ ሽብር” በይፋ ታወጀ፡፡ “ነጻ እርምጃ” ተፈቀደ፡፡
   
    በወቅቱ የኢህአፓው ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ አዲስ አበባ ውስጥ እንደነበረ ደርጎች ያውቁ ነበር፡፡ ነገር ግን አድራሻውን በትክክል ማወቅ አልቻሉም፡፡ ኢህአፓም ከጥር ወር መጨረሻ ጀምሮ እየተባባሰ በመሄድ ላይ የነበረውን የደርግ እርምጃ ለመቀልበስ እንደማይችል አውቆታል፡፡ ይሁንና የከተማውን የትጥቅ አመጽ አላቋረጠም፡፡ ደግሞም ዋና መሪውን ከደርግ አፍንጫ ስር አውጥቶ ከደህና ቦታ ለማድረስ አልሞከረም፡፡
  
   ታዲያ ኢህአፓዎች መሪአቸው ከከተማው ወጥቶ ለደህንነቱ አስተማማኝ በሆነ ቦታ ቢደበቅ ይፈልጉ ነበር፡፡ በተለይ በመጋቢት ወር አጋማሽ (1969) ከሚካሄደው የቤት ለቤት አሰሳ ነፍሱን እንዲታደግ ይመኙ ነበር፡፡ ይሁንና መሪው ከከተማው ለመውጣት ምንም ዓይነት ፍላጎት አልነበረውም፡፡ “በዚህ ክፉ ቀን ተከታዮቼን ጥዬ ከከተማ አልሰደድም” በማለት ቆርጧል፡፡ አሰሳ&#4813


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—-
    በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ (ከ1989-እስከ 1992 በነበረው ጊዜ) “ሐቄ” የምትባል ልጅ አውቃለሁ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት የሴቶች ጉዳይ ሃላፊ የነበረችው (በኋላ በኮትዲቯር የኢትዮጵያ አምባሳደር የሆነችው) ወ/ሮ ታደለች ሀይለሚካኤል የዚያች ልጅ እናት እንደነበረች ይወሳ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ የባለስልጣን ልጅ መሆኗን በመፍራት ብቻ ብዙዎች አይጠጓትም ነበር፡፡ ከልጅቷ ጋር የሚቀራረበው ተወልደ መዝገቡ የሚባል የአዲግራት ልጅ ብቻ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡
    
     የዩኒቨርሲቲው ትምህርት ከተጠናቀቀ ከጥቂት ወራት በኋላ መጽሔቶችን ሳገላብጥ ያቺ ልጅ ለምልክት ከሞት የተረፈች የፈጣሪ ተአምር እንደሆነች ተረዳሁ፡፡ አባቷ ነፍሲያውን ሊጠነቅ በተቃረበበት ወቅት ታሪኩን ትመሰክር ዘንድ የዘራት ብቸኛ ፍሬው ነበረች፡፡ ብዙዎች በእናቷ ሆድ የነበረችበትን ጊዜ በብዕራቸው ነካክተውታል፡፡ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም በበኩላቸው ያቺ ነፍስ በእናቷ ሆድ ውስጥ በመገኘቷ እናቷን ከሞት ያተረፈች መሆኗን መስክረውላታል፡፡ ለዚህም ይመስላል እናቷ “ሐቄ” የሚለውን ስም የሰጠቻት፡፡
ህይወት ተፈራ Tower in the sky የተባለውን መጽሐፍ ስትጽፍ ለዚያች ልጅ መጠነኛ ሽፋን ሰጥታለች፡፡ ከእናቷ ጋር የተነሳችውንም ፎቶግራፍ በመጽሐፉ ውስጥ አካተዋለች፡፡
                                                                          *****
   በፎቶግራፉ ላይ የምትመለከቱት የዚያች ልጅ አባት የነበረውን ሰው ነው፡፡ ይህ ሰው ከታሪካዊው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ መሪዎች መካከል አንዱ የነበረውና የመጀመሪያው የኢህአፓ ዋና ጸሓፊ ሆኖ የተመረጠው ብርሀነ መስቀል ረዳ ነው፡፡ ለብዙሃን ህይወት መለወጥ በብርቱ የታገለ፣ ሁለቱን ጠንካራ ስርዓቶች ፊት ለፊት የተጋፈጠ፣ ላመነበት ዓላማ ትምህርቱን ሰውቶ መታገልን የመረጠ፣ ከሀገር ወጥቶ በሰው ሀገርና በበረሃ የተንከራተተ፣ በመጨረሻ ላይ ግን ከገዛ ጓዶቹ ጋር ተጣልቶ የራሱን መንገድ የመረጠ፣ በዚህም ከፍተኛ የውዝግብ ርዕስ ለመሆን የበቃ የዚያ ዘመን ፋኖ!…
 
  ብርሀነ መስቀል ማን ነው?… በኢትዮጵያ ህዝቦች የፖለቲካ ትግል ውስጥ ምን ሚና ነበረው?… የርሱ ህይወትና የትግል መንገድ እንዴት ይገመገማል?… እነኝህ በኔ አቅም የሚመለሱ ጥያቄዎች አይደሉም፡፡ ታሪኩ እስከ አሁን ድረስ እያወዛገበ ስለሆነ ሐቁን ከግርድፉ ማጣራቱ ከባድ ጥረት ይጠይቃል፡፡ ብርሀነ መስቀል በወዳጆቹም ሆነ በጠላቶቹ የሚከበርና የሚፈራ መሆኑን ግን ማንም አያስተባብልም፡፡ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማሪያም በእስር ቤት አናዝዘውት ከገደሉት በኋላ “የመርሐቤቴ ገበሬዎች ገደሉት” እያሉ ለመዋሸት ቢሞክሩም በኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ውስጥ የነበረውን ሚና በአዎንታዊ መልኩ ነው የገለጹት፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የቅርብ ጓደኛው የነበሩት አንጋፋው ገጣሚና ባለቅኔ ኃይሉ ገብረ-ዮሐንስ (ገሞራው) “ችኩል እና ቁጡ ከመሆኑ በስተቀር ለሀገር መሪነት የሚበቃ ስብዕና ነበረው” በማለት መስክረውለታል፡፡
      ከሁሉም በላይ የብርሀነ መስቀልን ቆራጥነትና ልዩ ተሰጥኦ ሰፋ ባለ ሁኔታ የገለጹት የኢህአፓው ክፍሉ ታደሰ ነበሩ፡፡ አቶ ክፍሉ “ያ ትውልድ” በተሰኘውና በከፍተኛ ደረጃ ተነባቢ ለመሆን በበቃው መጽሐፋቸው “ብርሀነ መስቀል በኢህአፓ ውስጥ የራሱን አንጃ ፈጥሯል” የሚል ክስ እያቀረቡበት እንኳ ለትግሉ ያበረከተውን አስተዋጽኦ በተዋቡ ቃላት ገልጸዋል፡፡  ለምሳሌ ያህል የሚከተለውን መጥቀስ ይቻላል፡፡
    “በተማሪው እንቅስቃሴ ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከተውና አንደበተ ርቱእ የሆነው ብርሃነ መስቀል፣ በእንቅስቃሴው ውስጥ ሲታሰርና ሲፈታ የኖረ ነው” (ክፍሉ ታደሰ፣ ያ ትውልድ፣ ገጽ- 144)
                                                                          *****
    ብርሀነ መስቀል ለደርግ መርማሪዎች የሰጠው ቃል ሰሞኑን በኢንተርኔት ተበትኖ የብዙዎች መነጋገሪያ ሆኗል፡፡ እኔም ይህ 98 ገጾች ያሉት የምርመራ ቃል ከአንድ የፌስቡክ ጓደኛዬ ደርሶኝ እያነበብኩት ነው (ሙሉውን ዶክመንት www.debteraw.comከተሰኘ ዌብሳይት ማግኘት ትችላላችሁ)፡፡ እስከ አሁን ድረስ 1/3ኛ ያህሉን አገባድጄዋለሁ፡፡ ይሁንና ፊት ከማውቀው የብርሀነ መስቀል ታሪክ የተለየ ነገር አላገኘሁበትም፡፡ በሚቀጥሉት ቀናት አትኩሮት የሚስቡ መረጃዎችን ካገኘሁበት ልመለስ እችላለሁ፡፡ እስከዚያው ግን ስለብርሀነ መስቀል በትንሹ ላውጋችሁ፡፡
   ብርሃነ መስቀል ረዳ ወልደ-ሩፋኤል በ1930ዎቹ አጋማሽ በትግራይ ገጠር ነው የተወለደው፡፡ ያደገው ግን በደሴ ከተማ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ በነበሩት አጎቱ ቤት ነው፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደሴ በሚገኘው የወይዘሮ ስሒን ት/ቤት ካጠናቀቀ በኋላ በ1955 ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቷል፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታው ትምህርቱን ከመከታተል ይልቅ ተማሪዎችን ለተቃውሞ በማንቀሳቀሱ ላይ ነበር ያተኮረው፡፡ በዚህም መሰረት ወደ ዩኒቨርሲቲው እንደገባ ከርሱ ቀደም ብለው “አዞዎቹ” በሚል ቡድን ዙሪያ የተሰባሰቡትን የስር-ነቀል ለውጥ ደጋፊ ተማሪዎችን ለመቀላቀል በቅቷል፡፡ ከዓመት በኋላ በ1956 በዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ተማሪዎች ህብረት ውስጥ የመረጃ ኦፊሰር ሆኖ ተመርጧል፡፡ በአመቱ ደግሞ የብሔራዊ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ህብረት ዋና ጸሓፊ ሆኖ ነበር፡፡
Berhane Mesqel Redda
    
ብርሃነ መስቀል በ1957 የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች “መሬት ላራሹ” የሚል መፈክር አንግበው ድምጻቸውን ለፓርላማ ያሰሙበትን ታሪካዊ ሰልፍ ካደራጁት መካከልም ነበር፡፡ በዚያ ሰልፍ ሳቢያ ከትምህርታቸው ከተባረሩት ዘጠኝ ተማሪዎች መካከልም አንዱ ነው (በወቅቱ ከርሱ ጋር የተባረሩት ገብሩ ገብረወልድ፣ ሀይሉ ገብረዮሐንስ፣ ዮሐንስ ስብሐቱ፣ ታዬ ጉርሙ፣ ዘርዑ ክህሸን፣ ስዩም ወልደ ዮሐንስ፣ ሀብቴ ወልደ ጊዮርጊስና ሚካኤል አበበ ናቸው)፡፡ እነዚያ ተማሪዎች ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ዩኒቨርሲቲው ቢመለሱም በተረጋጋ ሁኔታ ትምህርታቸውን መከታተል አልቻሉም፡፡ በየጊዜው በሚካሄዱት ሰልፎችና የተቃውሞ ስብሰባዎች ግንባር ቀደም ተጠያቂ እየሆኑ ይታሰሩ ነበር፡፡ በስተመጨረሻ ግን የ“አዞዎቹ” ቡድን አባላት ከነአካቴው ከዩኒቨርሲቲው ተባረሩ፡፡ በመሆኑም በተደራጀ ሁኔታ ለመታገል ወሰኑ፡፡
   
   በዚህም መሰረት ብርሃነ መስቀልና አምስት ጓደኞቹ ከባህር ዳር ወደ አዲስ አበባ የሚበር አንድ አውሮፕላን በመጥለፍ ወደ ካርቱም ኮበለሉ፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላም ወደ አልጄሪያ ተሻገሩ፡፡ በአልጀርስ ቆይታቸው እጅግ ቀስቃሸ የሆኑ ጽሑፎችን እያዘጋጁ ወደ ሀገር ቤት ይልኩ ጀመር (በዚያ ዘመን “ጥላሁን ታከለ” በሚል የብዕር ስም በመጠቀም አስደናቂ ጽሑፎችን ይጽፍ የነበረው ብርሃነ መስቀል ረዳ እንደሆነ ነው የሚታመነው)፡፡ በአልጄሪያ የነበሩት ስደተኛ አብዮተኞች በውጪው ዓለም ትምህርታቸውን ከሚከታተሉ ኢትዮጵያዊያን ጋር በሚያደርጓቸው ግንኙነቶች በተደራጀ መንገድ የሚታገሉበትን መንገድ ቀየሱ፡፡ እነዚያ ውይይቶች እያደጉ ሄደው በ1964 ኢህአድ (የኢትዮጵያ ህዝብ አርነት ድርጅት) የተሰኘ ህቡዕ ፓርቲ ተወለደ፡፡ ብርሀነ መስቀል ረዳም የድርጅቱ ዋና ጸሐፊ ሆኖ ተመረጠ (የድርጅቱ ስም በ1967 “የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ” በሚል ተለውጧል፤ ይህም በአህጽሮት “ኢህአፓ” የሚባለው ነው)፡፡
     ብርሀነ መስቀል የኢህአድ ዋና ጸሓፊ በነበረበት የመጀመሪያ ዓመት በአብዛኛው ፓርቲውን የማስተዋወቅና ድጋፍ የመፈለግ ስራዎችን ነበር የሰራው፡፡ በዚህም ከአውሮፓ እስከ መካከለኛው ምስራቅ ድረስ ተጉዟል፡፡ ከባለቤቱ ታደለች ሀይለሚካኤል ጋር የተዋወቀው በዚያን ጊዜ ነው፡፡ በ1966 ብርሃነ መስቀልና ጥቂት ሰዎች የድርጅቱን የትጥቅ ትግል እንዲጀምሩ ወደ ኤርትራ ተላኩ፡፡ ወታደራዊ ስልጠና ለመውሰድ ለአንድ ዓመት በኤርትራ ከቆዩ በኋላ በ1967 መጀመሪያ ላይ ትግራይ ውስጥ ወደሚገኘው አሲምባ ተራራ ተሻገሩ፡፡ ሆኖም የትጥቅ ትግሉን ሳይጀምሩ በአሲምባ ቤዛቸው ለስድስት ወራት ቆዩ፡፡ በዚህ መሀል ስምንት ያህል የቡድኑ አባላት ከብርሀነ መስቀል ጋር የነበራቸውን ቀየሜታ በማሳበብ ድርጅቱን ጥለው ለደርግ መንግሥት እጃቸውን ሰጡ፡፡ ብርሀነ መስቀል በፋኖዎቹ አድራጎት በመቆጣቱ በሌሉበት የሞት ፍርድ ፈረደባቸው፡፡ ሆኖም ይህ ውሳኔው ከሌሎች የኢህአፓ አባላት ተቃውሞ ገጠመው፡፡ የኢህአፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጉዳዩን ካጣራ በኋላ በሰዎቹ ላይ የተላለፈው የሞት ፍርድ እንዲነሳ ወሰነ፡፡ ብርሀነ መስቀልም ከሰራዊቱ ተነጥሎ ወደ አዲስ አበባ እንዲሄድ ተወሰነ፡፡ ይህም በብርሀነ መስቀልና በሌሎቹ የኢህአፓ መሪዎች መካከል ንትርክ ፈጠረ፡፡
     ይህ በእንዲህ እንዳለ በነሐሴ ወር 1967 አህአፓ ራሱን በአዲስ መልክና በአዲስ ስም ሲያደራጅ “ዋና ጸሐፊ” የሚባል የስልጣን እርከን ተሰረዘ፡፡ ድርጅቱ ሊቀመንበርም ሆነ ዋና ጸሐፊ የለውም ተብሎ ታወጀ፡፡ ብርሀነ መስቀል ይህንን እርምጃ እርሱን ከቦታው ለማንሳት የተሸረበ ሴራ አድርጎ ስለወሰደው ከፍተኛ ቅሬታ አደረበት፡፡ ከማዕከላዊ ኮሚቴው ጋር የሚያደርገውንም ግንኙነት ማቀዝቀዝ ጀመረ፡፡ የደርግ መንግሥት በሚያዚያ ወር 1968 በህቡዕ ለተደራጁ ድርጅቶች ሁሉ የግንባር ጥሪ ሲያደርግ ብዙሃኑ የኢህአፓ አመራር ጥሪውን በመሰረቱ እንደሚቀበል ከገለጸ በኋላ መሟላት ያለባቸውን ቅድመ ሁኔታዎች አስቀመጠ፡፡  እነዚያ ሁኔታዎች ካልተሟሉ በስተቀር ከደርግ መንግሥት ጋር እንደማይሰራ ገለጸ፡፡ ብርሀነ መስቀል ግን “ቅድመ- ሁኔታ ማስቀመጡ ልክ አይደለም” በማለት ተከራከረ፡፡ በነሐሴ ወር 1968 የኢህአፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ “ራሳችንን ለመከላከል የከተማ ትጥቅ ትግል ማድረግ አለብን” በማለት ሲወስን ብርሀነ መስቀል “ውሳኔው አደገኛ ነው፤ ኢህአፓን ያስመታል፤ ደግሞም ደርግ ማርክሳዊ ነኝ ብሎ ያወጀ መንግሥት ስለሆነ ማርክሳዊ መንግሥትን በትጥቅ አመጽ መቃወም የአብዮታዊያን ጸባይ አይደለም” በማለት በብርቱ ተቃወመው፡፡ ይህም ታቃውሞ ከኢህአፓ አመራር ጋር እስከ ወዲያኛው አቆራረጠው፡፡
 
   የኢህአፓ አመራር ብርሀነ መስቀል ያሳያቸውን የአቋም ልዩነቶች ከገመገመ በኋላ ከማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነቱ ሰረዘው፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላም “ብርሀነ መስቀል በፓርቲው ውስጥ የራሱን አንጃ ለመመስረት ጥረት እያደረገ ነው” የሚል ክስ አቀረበበት፡፡ በድርጅቱ ጋዜጦች ላይ ግለ-ሂስ እንዲያደርግም አዘዘው፡፡ ብርሀነ መስቀልም ሂሱን ካወረደ በኋላ በድርጅቱ ታጣቂዎች እንዲጠበቅ ተደረገ፡፡ በሚያዚያ 1969 ግን ለማንም ግልጽ ባልሆነ መንገድ ከአዲስ አበባ ከተማ ተሰውሮ ወደ መርሐቤቴ አውራጃ ገባ፡፡ እዚያም ከተወሰኑ ሰዎች ጋር የትጥቅ ትግል ለማድረግ ሞከረ፡፡ ይሁን እንጂ በእርምጃው ከጥቂት ወራት በላይ አልዘለቀም፡፡ የደርግ አዳኝ ሀይሎች በ1970 መጀመሪያ ላይ ይዘውት ወደ አዲስ አበባ አመጡት፡፡ ለአንድ ዓመት ከሰድስት ወራት ያህል በታላቁ ቤተ መንግሥት ከታሰረ በኋላ በሚስጢር ተገደለ፡፡
                                                                          *****
      የብርሀነ መስቀል አንጃ የመፍጠር ሙከራ በራሱም አንደበት የተረጋገጠ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ብርሀነ መስቀል “እኔ ያካሄድኩት የእርማት ንቅናቄ እንጂ ፓርቲውን ለማጥፋት ያለመ አንጃ አልፈጠርኩም” ባይ ነው፡፡ በተጨማሪም ባለቤቱ ወይዘሮ ታደለች ሀይለ ሚካኤል በአንድ ወቅት በሰጡት ቃለ ምልልስ ብርሀነ መስቀል የእርማት ንቅናቄ ለማካሄድ መሞከሩን ተናግረዋል፡፡ በዚያ ዘመን በርሱ ስም የተሰራጩትን ልዩ ልዩ ዶክመንቶች በሙሉ የርሱ ናቸው ለማለት ይከብዳል፡፡ አንደኛው ጽሑፍ ግን በርሱ እጅ ጽሑፍ የተጻፈ መሆኑ ስለሚታወቅ የርሱን እምነት ይገልጻል ተብሎ ይታመናል፡፡ ብርሀነ መስቀል በዚያ ጽሑፉ የኢህፓን አመራር ቢኮንንም ደርግንም በሚገባ ይቃወማል፡፡ እንዲሁም በርሱ ስም ድርጅቱን የበጠበጡ በርካታ ቅጥረኞች እንደነበሩም ያወሳል፡፡ ሆኖም የኢህአፓ አመራር እርሱ ያለውን አምኖ የተቀበለው አይመስልም፡፡ ኢህአፓዎች “ለድርጅቱ ብተና ፈር የቀደደ ከሀዲ ነው” ነው የሚሉት፡፡
   ማንም የማይክደው አንድ ሐቅ ግን አለ፡፡ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ሲነሳ ብርሀነ መስቀልን መርሳት በጭራሽ አይሞከርም፡፡ በርካታ የለውጥ ፈላጊው ትውልድ አባላት የርሱን አርአያ በመከተል ወደ ትግሉ ጎራ መቀላቀላቸውንም ማስተባበል አይቻልም፡፡ ስለዚህ ምሁራን በቅጡ ያልተመረመውን የዚህን ፋኖ ታሪክ ጎልጎለው በትግሉ ውስጥ የነበረውን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ሚና ሳይሸፋፍኑ ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል፡፡
                                                                          *****
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 28/2006


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
  ተነገወዲያ ህዳር ህዳር 29/2007 ዘጠነኛው የብሄርና ብሄረሰቦች ቀን ሊከበር ነው፡፡ ይህ ቀን ለበዓሉ አከባበር የተመረጠው የኢፌዴሪ ህገ-መንግሥት የጸደቀበት ስለሆነ ነው ተብሏል፡፡ ታዲያ በዚሁ ቀን አንድ ታላቅ አብዮታዊ ተገድሎ ነበር፡፡ የሚገርመው ደግሞ በዚያች ቀን የሞተው ሰውዬ በኢትዮጵያ ውስጥ የብሄርና ብሄረሰቦች መብት መከበር አለበት በማለት ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ የጻፈ ሰው መሆኑ ነው፡፡
                                                                          *****
      ህዳር 29/1964፡፡ ረፋዱ ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ቦይንግ 708 ጄት አውሮፕላን ከአዲስ አበባ በአስመራ በኩል ወደ አቴንስ ሊበር ነው፡፡ በአውሮፕላኑ የሚጓዙ መንገደኞች ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል፡፡ ሰባት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችም ከአውሮፕላኑ ውስጥ ተሳፍረዋል፡፡ የበረራው ሰዓት ሲደርስ አውሮፕላኑ ከመሬት ተነሳ፡፡ ከሰማዩ ገብቶ መብረር ሲጀምር ግን ያልታሰበ ሁኔታ ተከሰተ፡፡ እነዚያ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አውሮፕላኑን በቁጥጥራቸው ስር ማዋላቸውን አስታወቁ፡፡  እነርሱ ወደሚፈልጉት ሀገር እንዲበሩም አብራሪዎቹን አዘዟቸው፡፡ ተማሪዎቹ የጠለፋ እወጃውን ካሰሙ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ሌላ ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡ አውሮፕላኑን ከጠለፋ እንዲታደጉ የታዘዙ ኮማንዶዎች በቀጥታ በጠላፊዎቹ ላይ በማነጣጠር ተኮሱባቸው፡፡ ስድስት ጠላፊዎች ተገደሉ፡፡ አንዲት ጓደኛቸው ደግሞ በከባድ ሁኔታ ቆሰለች፡፡ የአውሮፕላኑ ወለል በሙታኑ ደም ታጠበ፡፡
Walelign Mekoneen
                                                                          *****
    በዚያች ዕለት የሞተው ታዋቂው የተማሪዎች ንቅናቄ መሪ ዋለልኝ መኮንን ነበር፡፡ ከርሱ ጋር የተገደሉትም ማርታ መብራህቱ፣ ጌታቸው ሀብቴ፣ ተስፋዬ ቢረጋ፣ ዮሐንስ በፈቃዱ እና አማኑኤል ዮሐንስ ናቸው፡፡ እነዚያ ወጣቶች አውሮፕላኑን ለመጥለፍ የሞከሩት የስርዓቱ ክትትል መፈናፈኛ ስላሳጣቸው ነው፡፡ ዓላማቸው ወደ ውጪ ከኮበለሉት ጓደኞቻቸው ጋር በመቀላቀል ለስር-ነቀል ለውጥ የሚታገል ድርጅት መመስረት ነበር፡፡ ከድርጅቱ ምስረታ በኋላም ወደ ሀገር ቤት ተመልሰው ትግሉን በየአቅጣጫው ለማፋፋም አስበዋል፡፡ ሆኖም እንደተመኙት አልሆነላቸውም፡፡ አውሮፕላን ለመጥለፍ ማቀዳቸው ቀደም ብሎ ተጠቁሞ ስለነበር የጸጥታው ክፍል በአየር ላይ አፍኖ አስቀራቸው፡፡
                                                                          *****
     ከላይ በተገለጸው አሳዛኝ ገቢር (ትራጄዲ) ህይወቱ የተቋጨው ዋለልኝ መኮንን በወሎ ክፍለ ሀገር የሳይንት (ቦረና) አውራጃ ተወላጅ ነው፡፡ የአንደኛና ደረጃ ትምህርቱን በደሴው ንጉሥ ሚካኤል ትምህርት ቤት አጠናቀቀ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱንም እስከ አስረኛ ክፍል ድረስ ደሴ ከተማ በሚገኘው ታሪካዊው ወይዘሮ ስሒን ት/ቤት ተከታለለ፡፡ አስራ አንደኛና አስራ ሁለተኛ ክፍልን ደግሞ የዘመኑ ምርጥ ተማሪዎች መማሪያ በነበረው በአዲስ አበባው በዕደማሪያም ትምህርት ቤት አገባደደ፡፡ በ1958 ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከገባ በኋላም እጅግ የተለየ አብዮታዊ ሆነ፡፡
ዋለልኝ በ1959 በዩኒቨርሲቲው በተደረገው የግጥም ውድድር “ሙት ወቃሽህ መጣው” በሚለው ግጥም አንደኛ ወጥቷል፡፡  በዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ህብረት ይዘጋጅ በነበረው የታገል መጽሔት ከማንም በላይ የነቃ ተሳትፎ ያደርግ ነበር፡፡ በህቡዕ የሚዘጋጁ ጽሑፎችንም እያዘጋጀ ያሰራጭም ነበር፡፡ በተለይ “አዞዎቹ” የሚባለው የስር-ነቀል ለውጥ ደጋፊ የተማሪዎች ስብስብ በአቋም ደረጃ የተስማማባቸውን ሀሳቦች በጽሑፍ እያቀናበረ የሚያዘጋጀው እርሱ እንደነበር በያኔው እንቅስቃሴ የተሳተፉትም ሆነ የዘመኑን ታሪክ ያጠኑ ምሁራን ይመሰክራሉ፡፡
 
   ከዋለልኝ ጽሑፎች መካከል  ዝነኛ የሆኑት ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው ከላይ የጠቀስኩትና ህዳር 10/1961 በታተመው “ታገል መጽሔት” ላይ የወጣው “የብሄረሰቦች ጥያቄ በኢትዮጵያ” የሚል ርዕስ ያለው ጽሑፍ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ1962 የተማሪዎች ህብረት ፕሬዚዳንት የነበረው ጥላሁን ግዛው ሲገደል የአጼው ስርዓት በተማሪዎቹ ላይ ያደረገውን ዛቻ በመቃወም “ለአዋጁ አዋጅ” በሚል ርዕስ በህቡዕ ጽፎ የበተነው ጽሑፍ ነው፡፡ ዋለልኝ በጽሑፎቹ ሳቢያ በተደጋጋሚ ጊዜያት ታስሯል፡፡ በተለይ “ለአዋጁ አዋጅ”ን የጻፈው እርሱ መሆኑ ሲታወቅ በችሎት ፊት ቀርቦ አምስት ዓመት እስራት ተፈርዶበታል (ሆኖም ተማሪዎች ባደረጉት ከፍተኛ የተቃውሞ ጫና ከዓመት በኋላ ተፈትቷል)፡፡
     ከ1962 በኋላ ሁለት ክስተቶች የተማሪውን ንቅናቄ አቅጣጫ ቀይረውታል፡፡ እነዚህም በስርዓቱ የሚደረገው አፈና መጠናከር እና የድርጅት ምስረታ ጥያቄ መቀስቀስ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደ ቀድሞው ጊዜ የተቃውሞ ሰልፍ ከማድረግ ይልቅ የጥናት ክበቦችን እየመሰረቱ መወያየቱን መረጡ (የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በተቃውሞ ቀጠሉ)፡፡ ዋለልኝም በውይይት ክበቡ በሚያደርገው ጥናት ላይ አተኮረ፡፡ ከሀገር ተሰደው በአልጄሪያ ከሚገኙት እነ ብርሀነ መስቀል ረዳ ጋር በሚያደርገው የደብዳቤ ልውውጥ አማካኝነትም ሰፊ መሰረት ያለው ድርጅት ለመመስረት በሚደረገው ውይይትም ውስጥ ይሳተፍ ነበር፡፡ ህዳር 29/1964 በውጪ ካሉት ጓደኞቹ ጋር ለመቀላቀል ሲል አውሮፕላን ጠለፈ፡፡ ሆኖም ካሰበው ስፍራ ሳይደርስ በአውሮፕላኑ ውስጥ ተገደለ፡፡
                                                                          *****
     ከያኔው የተማሪዎች ንቅናቄ መሪዎች መካከል ዋለልኝ መኮንን ልዩ የሚያደርገው አንድ ነገር አለ፡፡ ይኸውም የተለያየ አመለካከት ባላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች እንደ ታላቅ ሰማዕት የሚታይ መሆኑ ነው፡፡ ደርግ፣ ኢህአፓ፣ ህወሐት፣ ኦነግ፣ ሻዕቢያ፣ መኢሶን፣ ወዘተ… ሁሉም ለርሱ በጎ አመለካከት ነው ያላቸው፡፡ ታዲያ በዋለልኝ ታሪክ ላይ የሚደረገው ሽሚያም በጣም የጠነከረ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ታሪኩን ከራሳቸው ድርጅት ጋር ለማቆራኘት ይሞክራሉ፡፡ በወቅቱ የነበረው የርሱና የጓደኞቹ አሰላለፍ ሲገመገም ግን ዋለልኝ ኢህአፓን ከመሰረቱ ወጣቶች ጋር ተመሳሳይ የፖለቲካ መስመር የነበረው ሆኖ ነው የሚታየው፡፡ ኢህአፓን የመሰረቱትም የርሱ የቅርብ ጓደኞች ናቸው፡፡ በመሆኑም ዋለልኝ በህይወት ቢሰነብት ኖሮ የዚሁ ድርጅት አባል ይሆን ነበር ተብሎ ነው የሚገመተው፡፡
                                                                          *****
ዋለልኝ መኮንን ከብዙ በጥቂቱ ይህ ነበር፡፡ ወደፊት ሰፋ ባለ ሁኔታ ስለርሱ እጽፋለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ እናንተም በበኩላችሁ የምታውቁትን እንድታጋሩን በአክብሮት እንጠይቃችኋለን፡፡
——                                                        
ሰላም
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 29/2006



(አፈንዲ ሙተቂ)
——
  በ19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ ነው፡፡ በታላቋ ብሪታኒያ ዋና ከተማ፡፡ በጊዜው አንድን አስገራሚ ገጸ-ባህሪ ያማከለ ተከታታይ የምርመራ ልብ ወለድ የሚጽፍ ወጣት ደራሲ ነበር፡፡፡ ታዲያ ይህ ደራሲ በዚያ ገጸ-ባህሪው ላይ ለአስር ዓመታት ከጻፈ በኋላ “ኤጭ! ይሄ ሰውዬ አሁንስ እጅ እጅ አለኝ፡፡ ስራ አስፈታኝ እኮ አቦ!… ከዚህ በኋላ ገድዬው ልረፍና ሌላ ድርሰት ልጻፍ” በማለት እራሱ የፈጠረውን ገጸ ባህሪ ይገድለዋል፡፡
 
     ይሁንና ገጸ-ባህሪውን የገደለው ደራሲ እንደተመኘው ሌሎች ድርሰቶችን በሰላም ሊጽፍ አልቻለም፡፡ ሺህ ምንተሺህ ደብዳቤዎች ከየአቅጣጨው ጎረፉለት፡፡ “አንተ ቀፋፊ፣ የማትረባ ወስላታ፣ አረመኔ ነህ” እየተባለ ተወቀሰ፤ ተወገዘ፡፡  “እኛ የምንወደውን ሰውዬ ገድለህ በሰላም መኖር አትችልም! አንተም ዋጋህን ታገኛታለህ” የሚሉ ማስፈራሪያዎችም እየተከታተሉ ደረሱት፡፡ በማስከተልም በሺህ የሚቆጠሩ አንባቢያን በለንደን ጎዳናዎች ላይ ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ደራሲው የገደለውን ገጸ-ባህሪ ከሞት እንዲያስነሳው ጠየቁት፡፡
  ደራሲው በዚህ ጉዳይ ተጨነቀ፡፡ ተጠበበ፡፡ የህዝቡን ፍላጎት ካላሟላ አደጋ ሊከተለው እንደሚችል ገመተ፡፡ ስለዚህ ሳይፈልግ በግዴታ በራሱ ብዕር የገደለውን ገጸ-ባህሪ ነፍስ ዘርቶበት እንደገና ወደ ስነ-ጽሑፍ ዓለም መለሰው፡፡ ህዝቡም የተመኘውን በማግኘቱ “እፎይ!” አለ፡፡
                                                     *****
  ያ ሰላማዊ ሰልፍ የተወጣለት ገጸ-ባህሪ “ሼርሎክ ሆምዝ” (Sherlock Holmes) ይባላል፡፡ በስነ-ጽሑፍ ዓለም ምንጊዜም ከማይረሱ ልዩ ገጸ-ባህሪያት አንዱ ነው፡፡ ሼርሎክ ሆምዝ የግል ወንጀል መርማሪ ነው፡፡ የመንግሥት ባለስልጣናትም ሆኑ ግለሰቦች አዕምሮአቸውን ያስጨነቀ ወንጀል-ነክ ጉዳይ ሲያጋጥማቸው ወደ ቢሮው እየሄዱ ጉዳያቸውን ያዋዩታል፡፡ እርሱም ልዩ ልዩ ፍንጮችን እየተከተለ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ ውጤቱን ለባለጉዳዮቹ ያሳውቃል፡፡ በዚህም መሰረት ወንጀሉ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀለኛው ርቆ ሳይሄድ በቁጥጥር ስር እንዲውል ይደረጋል፡፡ ወንጀሉ ወደፊት ሊፈጸም የታቀደ ከሆነ ደግሞ ሼርሎክ ሆምዝ ወንጀሉ ከመፈጸሙ በፊት ወንጀለኛውን በቁጥጥር ስር ያውለውና ከነማስረጃው ለፖሊስ ያስረክባል፡፡
  ታዲያ ሸርሎክ ሆምዝ የሚፈጽማቸውን ጀብዱዎች የምንሰማው ከርሱ አንደበት አይደለም፡፡ የዕለት ተዕለት ውሎውን እየተከታተለ ለኛ የሚዘግብልን ዶ/ር ጆን ኤች ዋትሰን የሚባል ጓደኛው ነው፡፡ ዶ/ር ዋትሰን የሼርሎክ ሆምዝ የልብ ጓደኛ እና ሚስጢረኛው ነው፡፡ ሁለቱ ሰዎች ለብዙ ጊዜ አይለያዩም፡፡ አንድ ልዩ ኦፕሬሽን የሚካሄድ ከሆነ ሼርሎክ ሆምዝ ጓደኛው ዶ/ር ዋትሰን እንዲሳተፍበት ያደርጋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ዋትሰን ከሎንዶን ወደ አውሮጳ እየተላከ ሼርሎክ ሆምዝ የሚፈልጋቸውን መረጃዎች እንዲያሰባስብ ይደረጋል፡፡
 
    በዶ/ር ዋትሰን ገለጻ መሰረት ሼርሎክ ሆምዝ ቀጠን ዘለግ ያለ እንግሊዛዊ ነው፡፡ ቢሮው በደቡብ ለንደን በሚገኘው የቤከር ጎዳና ነው፡፡ አንዲት የነተበች ባርኔጣ ይለብሳል፡፡ አጭር ከዘራም ከእጁ አያጣም፡፡ ሼርሎክ ሆምዝ በጣም አጫሽ ነው፡፡ ፒፓውን ከአፉ የማይነጥል የትምባሆ ሱሰኛ! ደግሞ ግማሽ ጭልፋ የምታክል ሌንስ (አጉሊ መነጽር) ከኪሱ አትጠፋም፡፡ በርሷ ብዙ ነገሮችን ይመረምራል፡፡ በተለይም የሰው ዱካ የሚመረምረው በዚህች ሌንስ ነው፡፡ 
 
    የሼርሎክ ሆምዝ ወንጀል መርማሪነት እንዲህ ቀለል ያለ አይደለም፡፡ ኬሚካሎችንና ቅመማ ቅመሞችን በደንብ ለይቶ ያውቃል፡፡ የሲጋራዎችን አመድ በማየት ብቻ አንድ ሰው ምን ዓይነት ሲጋራ እንደሚያጨስ ለይቶ ያውቃል፡፡ ደግሞም ሼርሎክ ሆምዝ የጁዶ ጥበበኛ ነው፡፡ ወንጀለኞች ሊያጠቁት ከመጡ በጁዶ ይዘርራቸዋል፡፡ በመላው ለንደን በርካታ ሰላዮች አሉት፡፡ ሊስትሮዎች፣ ለማኞች፣ ጎዳና ተዳዳሪዎች፣ ሴተኛ አዳሪዎች፣ የባንክ ሰራተኞች ወዘተ… ልዩ ልዩ መረጃዎች እንዲያመጡለት ይቀጥራቸዋል፡፡ ከነዚህ ምንጮች በሚያገኛቸው መረጃዎች ላይ የራሱን የምርመራ ጥበብ እያከለ አስደናቂ ውጤቶችን ያገኛል፡፡
                                                     *****
    ሼርሎክ ሆምዝን የፈጠረው ደራሲ ሰር አርተር ኮናን ዶይል ይባላል፡፡ በዓለም የስነ-ጽሑፍ ታሪክ ዘወትር ከሚታወሱ ድንቅ ደራሲዎች አንዱ ነው፡፡ ኮናን ዶይል የስኮትላንድ ተወላጅ ነው፡፡ በጉርምስናው ዕድሜ ላይ ህክምናን ሊያጠና ኤዲንበርግ ዩኒቨርሲቲ ይገባል፡፡ ታዲያ እዚያ እያለ ፕሮፌሰር ጆሴፍ ቤል ከሚባሉት አስተማሪው ላይ ባየው ነገር በጣም ይመሰጣል፡፡ እኝህ ፕሮፌሰር ሀኪም ጭምር ናቸው፡፡ የህመምተኞችን በሽታ በትክክል ለማወቅ የሚጠቀሙበት የተጠየቅ (logic) አካሄድና ጥቃቅን የሆነችውን ነገር ሁሉ ለማወቅ የሚያደርጉት ጥረት በወጣቱ ተማሪ አርተር ኮናን ዶይል ላይ የማይረሳ ትውስታ ጥሎ ያልፋል፡፡
   
  ኮናን ዶይል ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ የራሱን ክሊኒክ ከፍቶ መስራት ይጀምራል፡፡ ነገር ግን ጀማሪ በመሆኑ የሚመጣለት በሽተኛ በጣም ትንሽ ነበር፡፡ ታዲያ ኮናን ዶይል አልሰነፈም፡፡ የመጡለትን በሽተኞች ካከመ በኋላ በሚኖረው ትርፍ ጊዜ ቁም-ነገር ለመስራት ወሰነ፡፡  በመሆኑም የዩኒቨርሲቲ አስተማሪውን ሁኔታ እያሰበ የሚመጣለትን ሃሳብ በወረቅ ጫር ጫር ማድረግ ጀመረ፡፡ የጻፈውንም The Study in the Scarlet የሚል ርዕስ ሰጠውና Beeton’s Christmas Annual  በተሰኘ መጽሔት ላይ አሳተመው፡፡
     ጽሑፉ “ሼርሎክ ሆምዝ” የተባለ ወንጀል መርማሪ በአስገራሚ የተጠየቅ ዘዴ ወንጀሎችን እንዴት እንደሚመረምር የሚተርክ አጭር ልብ ወለድ ነው፡፡ አንባቢያን ጽሑፉን ስለወደዱት The Strand የሚባል መጽሔት በቋሚነት የሼርሎክ ሆምዝን ታሪክ እንዲጽፍለት ቀጠረው፡፡ ደራሲው ኮናን ዶይልም ለአምስት ዓመታት ያለመሰልቸት የሼርሎክ ሆምዝን ታሪክ ጻፈ፡፡ በአምስተኛው ዓመት በታተመው አንድ ጽሑፍ ላይ ግን “ሼርሎክ ሆምዝ ሌሎች የልብ ወለድ ስራዎችን እንዳልጽፍ እያደረገኝ ነው” በማለት ገድሎት ሊገላገለው ወሰነ፡፡ The Final Problem የሚል ርዕስ የተሰጠው አጭር ልብ ወለድ ጻፈና ሼርሎክ ሆምዝን  በብዕሩ ገደለው፡፡ ደራሲው እንዲህ ሲያደርግ “ሼርሎክ ሆምዝ ሞቷል፤ ከእንግዲህ ታሪኩን አትጠብቁ” ማለቱ ነው፡፡
    ይሁንና ከላይ እንደገለጽኩት ህዝቡ በጄ አላለውም፡፡ “ሼርሎክ ሆምዝን ገድለህ አንተም በሰላም አትኖራትም!” በማለት ማስጠንቀቂያና ዛቻ ላከለት፡፡ ከዚህ ሌላም  ሃያ ሺህ የስትራንድ መጽሄት ቋሚ ደንበኞች (Subscribers) ደንበኝነታቸውን አቋረጡ፡፡ የእንግሊዝ ንጉሣዊያን ቤተሰብ ንዴቱንና ብስጭቱን ለደራሲው ገለጸለት፡፡ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ ኮናን ዶይልን ክሊኒኩ ድረስ ሄዶ ለመነው፡፡ “መጽሔታችን በኪሳራ ሊዘጋ ነው፤ ያ እንዳይሆን እባክህ ሼርሎክ ሆምዝን ከሞት ቀስቅሰውና ታሪኩን ጻፍልን” አለው፡፡
   ኮናን ዶይል የመጽሔቱ አዘጋጅ ቢሮው ድረስ ሲመጣበት ይሉኝታ ያዘውና “እምቢ!” ማለት አቃተው፡፡ ስለዚህ በዘዴ ላባርረው በማለት “በወር ሃያ አምስት ፓውንድ የምትከፍሉኝ ከሆነ እጽፋለሁ” በማለት በዘመኑ ተሰምቶ የማይታወቅ ከፍተኛ ክፍያ ጠየቀ፡፡ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ “አሳምሬ እከፍላለሁ! አንተ ብቻ ጻፍልኝ እንጂ” አለው፡፡ ኮናን ዶይል ከዚያ በፊትም ከህዝቡ የመጣበትን ዛቻ ፈርቶ ሼርሎክ ሆምዝን ሊቀሰቅሰው ወስኖ ስለነበረ የስትራንድ መጽሔት አዘጋጅ ክፍያውን ሲጨምርበት አዲስ ጉልበት አገኘ፡፡ በመሆኑም ሼርሎክ ሆምዝን ከሞት ሊያስነሳው ወሰነ፡፡ እናም “The Adventure of the Empty House” የሚል ርዕስ የሰጠውን ልብ ወለድ ጻፈና ዝነኛውን ገጸ-ባህሪ እንደገና ከሞት ቀሰቀሰው፡፡ አንባቢዎቹም ሼርሎክ ሆምዝ አለመሞቱን ሲረዱ በደስታ ፈነደቁ፡፡
      ታዲያ ኮናን ዶይል ሼርሎክ ሆምዝን የቀሰቀሰው እንዴት መሰላችሁ?….. ጓደኛው ዶ/ር ዋትሰን ቢሮው ውስጥ ሆኖ ሲተክዝ ቆፍጣናው ሼርሎክ ሆምዝ በድንገት ወደ ቢሮው ይገባል፡፡ ዋትሰን ዐይኑን ማመን አቃተው፡፡ ካለበት በደስታ ተነስቶ አቀፈው፡፡ ከናፍቆት ሰላምታ በኋላ ዋትሰን “ሞተሃል ተብሎ አልነበረም እንዴ?…” ይለዋል፡፡ ሼርሎክ ሆምዝም “ሆን ብዬ ያስወራሁት ወሬ ነው፡፡ በጋዜጣም ማስታወቂያ እንዲነገር ያደረግኩት እኔ ነኝ፡፡ አየህ! አንድ የምከታተለው አደገኛ ወንጀለኛ አለ፡፡ ያ ወንጀለኛ አልያዝ ብሎ አስቸግሮኛል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዱካው ጠፍቶብኝ ነበር፡፡ ስለዚህ መሞቴን በጋዜጣ አሳወቅኩ፡፡ እንደዚያ ያደረግኩት ወንጀለኛው መሞቴን ሲረዳ ከተደበቀበት እንደሚወጣ ስለማውቅ ነው” በማለት ትረካውን ይጀምርለታል፡፡ ከዚያም ዝርዝሩን አንድ በአንድ ለዶክተር ዋትሰን ያጫውተዋል፡፡ ከዚያች አጭር ልብ ወለድ በኋላም ሼርሎክ ሆምዝ እንደ አዲስ መነበብ ይጀምራል፡፡
                                                      *****
    አርተር ኮናን ዶይል የሼርሎክ ሆምዝን ድንቅ ምርመራዎች የሚተርኩ 56 አጫጭር ታሪኮችንና አራት ሙሉ ልብ ወለዶችን ጽፏል፡፡ እርሱ ከሞተ በኋላ ደግሞ ሼርሎክ ሆምዝ በሺህ በሚቆጠሩ ፊልሞች፣ ቲያትሮችና ልዩ ልዩ የጽሑፍ ውጤቶች ውስጥ ለጥበብ ታዳሚዎች ቀርቧል፡፡ በዓለም ዙሪያ በርካታ የሼርሎክ ሆምዝ ቡድኖች አሉ፡፡ በለንደን ከተማ በየዓመቱ ሁለት ጊዜ የሼርሎክ ሆምዝ ፌስቲቫል ይካሄዳል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ በሺህ የሚቆጠሩ ቱሪስቶች ሼርሎክ ሆምዝ ይኖርበታል ተብሎ የተጠቀሰውንና በቤከር ጎዳና የሚገኘውን የቤት ቁጥሩ 212B የሆነውን ህንጻ በየዓመቱ ይጎበኙታል፡፡ በህንጻው ውስጥ በሼርሎክ ሆምዝ አምሳል የተሰራ አዳፋ ኮፍያ የያዘ፣ ከዘራ ያነገተና ፒፓውን በአፉ የጎረሰ አርቲፊሻል ሰው ቆሞበታል፡፡
 
  ይህ ሁሉ ክብርና ፍቅር የሚሰጠው በምናብ ለተፈጠረ ገጸ-ባህሪ ነው፡፡ ክላሲክ የሚባሉት ጸሐፍት እንደ ሼርሎክ ሆምዝ ያሉትን ከሰው ልብ የማይጠፉ ልዩ ገጸ-ባህሪያትን የመፍጠር ብቃት ነበራቸው፡፡ ዣንቫልዣ፣ ዶን ኪኾቴ፣ አንክል ቶም፣ ራስኩልኒኮቭ፣ ሐምሌት፣ ኦቴሎ፣ ወዘተ የመሳሰሉ ገጸ-ባህሪያትን የሚያውቁ የስነ-ጽሑፍ አፍቃሪዎች ሼርሎክ ሆምዝንም ዘወትር ያስታውሱታል፡፡ እኛም ዘወትር እናስታውሰለዋን፡፡
ሰላም!
  —-
መጋቢት 26/2006
አፈንዲ ሙተቂ


 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
የውጪ ደራሲያን የጻፏቸውን መጻሕፍት ወደ አማርኛ መተርጎሙን ማን እንደጀመረው በትክክል አላውቅም፡፡ ሆኖም የዶ/ር ሳሙኤል ጆንሰን ድርሰት የሆነው “ራሴላስ” በአማርኛ የተተረጎመ የመጀመሪያው የውጪ መጽሐፍ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ ከዚያም ክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል የትርጉም ስራዎችን በስፋት ተያይዘውት ነበር፡፡ ለምሳሌ ከበደ ሚካኤል የሼክስፒርን ሮሚዮና ጁሌት በ1940ዎቹ ተርጉመውት ነበር፡፡ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህንም በርካታ የሼክስፒር ስራዎችን በ1960ዎቹ ተርጉመዋል፡፡
  
  የአማርኛ የትርጉም ስራዎች እንደ አሸን የፈሉት ግን “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት” በ1970ዎቹ ከተቋቋመ በኋላ ነው፡፡ በዚያ ዘመን በተለይም ዘመን አይሽሬ የሚባሉ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ ስራዎች በብዛት ወደ አማርኛ ተመልሰዋል፡፡ ኢ-ልቦለድ ከሆኑትም መካከል የካርል ማርክስን “ዳስ ካፒታል”ን ጨምሮ በርከት ያሉ መጻሕፍት ተተርጉመዋል፡፡
በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ ደግሞ የትርጉም ስራው የዳኒኤላ ስቴልን፣ የሲድኒ ሸልደንንና የአርቪንግ ዋላስን ስራዎች ወደ አማርኛ በመመለሱ ላይ ነበር ያተኮረው፡፡ እስከ 1990ዎቹ መጀመሪያ ድረስ በብዛት ሲተረጎሙ የነበሩት ደግሞ የጃኪ ኮሊንስ ድርሰቶች ናቸው፡፡ አሁን ግን የትርጉም ስራው ቀዝቅዟል፡፡
   ለመሆኑ እስከ ዛሬ ድረስ በአማርኛ የተተረጎሙ ታላላቅ የስነ-ጽሑፍ በረከቶች የትኞቹ ናቸው? ይህንን ጥያቄ መመለስ ይከብዳል፡፡ ቢሆንም የቻልኩትን ያህል ለመዘርዘር እሞክራለሁ፡፡ ታዲያ በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት በመላው ዓለም ዝነኛ ለመሆን የበቁ ስራዎች ብቻ ናቸው፡፡ ለምሳሌ የነ ዳንኤላ ስቴል፣ ሲድኒ ሸልደንና ጃኪ ኮሊንስ ስራዎች በሀገራችን በብዛት ቢተረጎሙም በዓለም ዙሪያ ያላቸው ተነባቢነት እምብዛም ነው፡፡
    መጻሕፍቱን የምጠራቸው በአማርኛው ርዕሳቸው ነው፡፡ የዋናውን ደራሲ ስም እና የተርጓሚውንም ስም እጠቅሳለሁ፡፡ በአንዳንድ የተርጓሚዎችን ማንነት ለማወቅ ስቸገር ግን ዝም ብዬ አልፌአቸዋለሁ፡፡
(ማስታወሻ፡ ይህ ዝርዝር የሃይማኖት መጻሕፍትን አይመለከትም)፡፡
==== ዘመን አይሽሬ የልብወለድ መጻሕፍት (Classical Fictions)===
1.      “ነገም ሌላ ቀን ነው”፣ ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል፣ ተርጓሚ ነቢይ መኮንን
2.     “መከረኞች”፣ ደራሲ ቪክቶር ሁጎ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም (በህይወቴ ያነበብኩት ምርጥ የአማርኛ ትርጉም ስራ ይህኛው ነው)፡፡
3.     “የሁለት ከተሞች ወግ”፣ ደራሲ ቻርለስ ዲከንስ፣ ተርጓሚ ሳህለ ሥላሤ ብርሃነማሪያም
4.     “የአገር ልጅ”፣ ደራሲ ሪቻርድ ራይት፣ ተርጓሚ ሳህለሥላሤ ብርሃነማሪያም
5.     “ዶን ኪኾቴ”፣ ደራሲ ሚጉኤል ሰርቫንቴስ፣ ተርጓሚ ዳምጤ አሰማኽኝ (ሌላ ሰው ይህንኑ መጽሐፍ “ዶን ኪሾት” በሚል ርዕስ ተርጉሞት ነበር፤ ይሁን እንጂ ያኛው ትርጉም ብዙም አይጥምም)
6.     “ሳቤላ”፣ ደራሲ ሄንሪ ውድ፣ ተርጓሚ ሀይለ ሥላሤ መሓሪ
7.     “እናት”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
8.     “ዩኒቨርሲቲዎቼ”፣ ደራሲ ማክሲም ጎርኪ
9.     “አጎቴ ቫኒያ”፣ አንቶን ቼኾቭ
10.    “ሼርሎክ ሆምዝ”፣ ደራሲ ሰር አርተር ኮናን ዶይል፣ ተርጓሚ ዳኛቸው ተፈራ
11.     “ውቢት”፣ ደራሲ አልቤርቶ ሞራቪያ፣ ትርጉም ሺፈራው ጂሶ
12.    የካፒቴኑ ሴት ልጅ፡ ደራሲ አሌክሳንደር ፑሽኪን
13.    “ካፖርቱ”፣ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
14.    እንደ ሰው በምድር እንደ አሳ በባህር፡ ደራሲ ኒኮላይ ጎጎል
15.    “ወንጀልና ቅጣት”፣ ደራሲ ፊዮዶር ዶስቶየቪስኪ፣ ተርጓሚ ካሳ ገብረህይወት እና ፋንቱ ሳህሌ
16.    “እንዲህ ሆነላችሁ”፣ ደራሲ ሩድያርድ ኪፕሊንግ፣ ተርጓሚ አረፈዐይኔ ሐጎስ
17.    “አሳረኛው”፣ ደራሲ ነጂብ ማህፉዝ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
18.    ሌባውና ውሾቹ፣ ደራሲ ነጂብ ማሕፉዝ፤
19.    “እፎይታ”፣ ደራሲ አሌክሳንደር ዱማስ ፔሬ፣
20.   “ጃኩሊን”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ
21.    “የደም ጎጆ”፣ ደራሲ አጋታ ክሪስቲ፣ ተርጓሚ ሌ/ኮሎኔል ጌታቸው መኮንን ሐሰን
22.   “አና ካሬኒና”፣ ደራሲ ሊዮ ቶልስቶይ፣
23.    “ሽማግሌውና ባህሩ”፣ ደራሲ አርነስት ሄሚንግዌይ፣
24.    “እሪ በይ አገሬ”፣ ደራሲ አላን ፒተን፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
25.    “የስዕሉ ሚስጢር”፣ ደራሲ ኦስካር ዋይልድ፣ ተርጓሚ ፋሲል ተካልኝ አደሬ
26.   “ጠልፎ በኪሴ”፣ ደራሲ ተውፊቅ አልሃኪም፣ ተርጓሚ መንግሥቱ ለማ
27.   “የእንስሳት እድር”፣ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል፣ ተርጓሚ ለማ ፈይሳ
===ዓለም አቀፍ የተረት መጻሕፍት===
1.       “ተረበኛው ነስሩዲን”፣ ደራሲ ኢድሪስ ሻህ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
2.     “አንድ ሺህ አንድ ሌሊት”፣ ወደ እንግሊዝኛ ተርጓሚ ሪቻርድ በርተን፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተፈሪ ገዳሙ
3.     “ጥንቸሉ ጴጥሮስ፣ ደራሲ ቤትሪክስ ፖተር፣
4.     “የኤዞፕ ተረቶች”፣ ደራሲ ኤዞፕ፣ ተርጓሚ አማረ ማሞ
5.     “የግሪም ተረቶች”፣ ደራሲ የግሪም ወንድማማቾች፣ ተርጓሚ ዓለም እሸቱ
====ዘመን አይሽሬ የግጥም ስብስቦች====
1.      “ነቢዩ”፣ ገጣሚ ካህሊል ጂብራን
2.     የአሌክሳንደር ፑሽኪን ግጥሞች፣ ተርጓሚ አያልነህ ሙላቱ
3.     የዑመር ኸያም ሩባያቶች፣ ወደ እንግሊዝኛ ትርጉም በኤድዋርድ ፊዝጂራልድ፣ ወደ አማርኛ ተርጓሚ ተስፋዬ ገሠሠ
4.     ኢሊያድ እና ኦዲሴይ፣ ገጣሚ ሆሜር፣ ተርጓሚ ታደለ ገድሌ
==== ወቅታዊ የሽያጭ ሪከርድ ያስመዘገቡ መጻሕፍት (Best Sellers)====
1.      “የጡት አባት”፣ ደራሲ ማሪዮ ፑዞ
2.     “የሚስጢሩ ቁልፍ”፣ ደራሲ ኬን ፎሌት፣ ተርጓሚ ኤፍሬም እንዳለ
3.     “የዳቪንቺ ኮድ”፣ ደራሲ ዳን ብራውን፣
4.     “ሃሪ ፖተር እና የፈላስፋው ጠጠር”፣ ደራሲ ጄ.ኬ. ሬውሊንግስ፣
5.      “ሳዳም ሑሴን እና የባህረ ሰላጤው ቀውስ”፣ ደራሲ ባሪ ሩቢን፣
6.     “ሞገድ”፣ ደራሲ አርቪንግ ዋላስ፣
7.     “የኦዴሳ ፋይል”፣ ደራሲ ፍሬድሪክ ፎርስይዝ፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
8.     “ዘጠና ደቂቃ በኢንቴቤ”፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     አስራ አንዱ ውልዶች፣ ደራሲ ጄፍሪ አርቸር፤
=== ዓለም አቀፍ ተጽእኖን የፈጠሩ የፖለቲካና የፍልስፍና መጻሕፍት===
1.      “ካፒታል”፣ ደራሲ ካርል ማርክስ፣ (በቡድን ነው የተተረጎመው፡፡ የጓድ መንግሥቱ ኃይለማሪያም አስተርጓሚ የነበሩት አቶ ግርማ በሻህ እና ደራሲ ስብሐት ገብረ እግዚአብሄር በተርጓሚዎቹ ውስጥ ይገኛሉ)፡፡
2.     “የኮሚኒስት ፓርቲ ማኒፌስቶ”፣ ደራሲ ካርል ማርክስና ፍሬድሪክ ኤንግልስ፣ ተርጓሚ “ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት”
3.     “የሌኒን ምርጥ ስራዎች”፣ ደራሲ ቪላድሚር ሌኒን፣ ተርጓሚ “ኩራዝ”
=== ታዋቂ ግለ-ታሪኮችና የታሪክ ማስታወሻዎች===
4.     “ትንሿ መሬት”፣ ደራሲ ሊዮኒድ ብሬዥኔቭ፣ ተርጓሚ “ፕሮግሬስ የመጻሕፍት ማዘጋጃ ድርጅት”
5.     “የኦሽዊትዝ ሚስጥር”
6.     የአና ማስታወሻ፤ ደራሲ “አና ፍራንክ”፣ ተርጓሚ “አዶኒስ”
7.     “ፓፒዮ”፣ ደራሲ ሄንሪ ቻሬሬ
8.     “በረመዳን ዋዜማ”፣ ደራሲ ሙሐመድ ሀይከል፣ ተርጓሚ ማሞ ውድነህ
9.     “የጽናት አብነት”፣ ሄለን ከለር
=== ሌሎች ኢ-ልብወለድ መጻሕፍት===
1.      “ጠብታ ማር”፣ ደራሲ ዴል ካርኒጌ፣ ተርጓሚ ባሴ ሀብቴና ደምሴ ጽጌ


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
እነሆ ከተሚማ ጋር የጂማን ምድር “ሽርርርር” ልንልበት ነው፡፡ ሆኖም “ተሚማ” የትናንትናው ሙገሳ አንሶኛል ብላለች፡፡ “የነየታችሁት ሐጃ ሞልቶላችሁ በደስታ እንድትፍለቀለቁ ካሻችሁ ሙገሳውን ጨመርመር አድርጉልኝ” ትላለች፡፡ ታዲያ እኛም አላንገራገርንም፡፡ “ምን ገዶን! አንቺ ሰኚ ሞቲ! ሙገሳ በየዓይነቱ ይኸውልሽ” ብለን በድጋሚ መወድሳችንን ልንደረድርላት ተዘጋጅተናል፡፡ እንዲያውም ሙገሳችንን የምንጀምረው እሸትነቷን በማወደስ ነው፡፡ ለመወድሳችን የመረጥነውም የሟቹን የዮሴፍ ገመቹን ዜማ ነው፡፡ አዝማቹ እንዲህ ይሄዳል፡፡
Naale naale naalen irgixiidhaa
Maddiin furnoo hidhiin buskutiidha.
በአማርኛ ሲተረጎም እንዲህ ይሆናል (አማርኛው አዛማጅ ትርጉም በመሆኑ የኦሮምኛውን ያህል አስደሳች ላይሆን ይችላል)፡፡
ናሌ ናሌ ናሌ እርግጥ ነው፡፡
ጉንጯ ፉርኖ ከንፈሯም ብስኩት ነው፡፡
ፈገግ ያሰኛል አይደል? (ቂቂቂቂቂ….)፡፡ አዎን! በኦሮምኛ እንዲህ እያሉ መግጠምም ይቻላል፡፡ መወድሱ ከወገብ በታች ያለውን የሰውነት ክፍል አይንካ እንጂ ከወገብ በላይ ያለውን ውበት በሚያውቁት መንገድ ማወደስ ይቻላል፡፡ ከወገብ በታች ካለው የሰውነት ክፍልም ተረከዝን ማሞገስ ይቻላል፡፡ ከዚያ በላይ ያለውን ክፍል ግን መጥቀስ አይፈቀድም፡፡
ዮሴፍ በግጥሙ ውስጥ “ናሌ ናሌ..” የሚል ሐረግ ደጋግሟል አይደል? ቃሉ እንዲህ ሲደጋገም ትርኪ ምርኪ ሊመስል ይችላል፡፡ ነገር ግን ያለቦታው የገባ አይምሰላችሁ፡፡ ትናንትና የጠቀስነው “አህለን አህላ” ነው ተቀይሮ እንዲህ የሆነው፡፡ ዘፋኙ ዘፈኑን የሚጀምረው በዚህ ሐረግ ነው፡፡ ከዚያም እርሱ የዘፈኑን ግጥሞች እያከታተለ ሲጠራ ተቀባዮቹ “ናሌ ናሌ…” እያሉ ጨዋታውን ያደምቁለታል፡፡
*****
አሁን ደግሞ የአማርኛ ተናጋሪዎችን በመወከል ተሚማን እናሞግሳታለን፡፡ ለሙገሳችን የመረጥነውም የነዋይ ደበበን “ከጊቤ ባሻገር”ን ነው፡፡
ከጊቤ ባሻገር አለችኧረ አንዲት ሰው
በፍቅር በናፍቆትልቤን የምትወዘውዘው
አቦል ጀባብላኝ ቡናዋን ብቀምሰው፣
እግሬ ወደጅማ ሱስ አመላለሰው
እንግባ አይመሽምወይ
ቤትሽ ጅማ ነውወይ ?
ነዋይ እውነታውን ነው ቁጭ ያደረገው፡፡ “ተሚማ” ቄጤማ ጎዝጉዛ፣ ቡናውን አፍልታ ሐድራውን ሞቅ ሞቅ ስታደርገው ፍቅር የምትፈትል ነው የምትመስለው፡፡ ከሐድራው የሚፈልቀው ሙሐባ የቡና ሱስ ብቻ ሳይሆን የፍቅር ሱስን ያስይዛል፡፡
ደግሞ አንድ ነገር!! በሌሎች አካባቢዎች እንግዳን በእቅፍ አበባ ነው የሚቀበሉት አይደል?… የጅማዋ ተሚማ ደግሞ ለዚያራ የመጣውን ሰው በቡና ቀንበጥ ነው የምትቀበለው፡፡ እንዲህ ያለች ጥበበኛ አርቲስት ናት ተሚማ!
*****
ኧረ ለመሆኑ እኛ እንዲህ ያሞገስናት “ተሚማ” በርግጥ ፍቅርን ታውቀዋለች?… ምንም አትጠራጠሩ!! ተሚማ ፍቅርን ከማወቅም አልፋ ለፍቅር የምትንበረከክ ልበ-ንጹህ ናት፡፡ ከልቧ ለምታፈቅረው ሰው ፍቅሯን የምትገልጸው ደግሞ በጣም ኪነታዊ በሆነ መንገድ ነው፡፡ ይህም “ሂዲ ደርቡ” (Hiddii darbuu) ይባላል:: “ሂዲ ደርቡ” የኦሮሞ ሴቶች ለፍቅር መረታታቸውን የሚገልጹበት ወግ ነው፡፡ ይህም በአማርኛ “ሎሚ መወርወር” ከምንለው ወግ ጋር ይቀራረባል፡፡ ልዩነቱ ግን ተሚማ ፍቅሯን በምትገልጽበት ጊዜ የምትወረውረው ነገር “ሎሚ” ሳይሆን “እምቧይ” ነው፡፡ ሁለተኛው ልዩነት ደግሞ “ሂዲ ደርቡ” እንደ “ሎሚ መወርወር” በጥምቀት ብቻ የሚፈጸም አለመሆኑ ነው፡፡ ሶስተኛው ልዩነት ተሚማ እምቧዩን ሌሎች ሰዎች እያዩዋት የምትወረውር አለመሆኑ ነው፡፡ Safuu የሚባለው የኦሮሞ የስነ-ምግባር ደንብ ይህንን እንዳታደርግ ያግዳታል፡፡ በመሆኑም ተሚማ የወደደችውን ሰው በእምቧይ የምትመታው ሰው በሌለበት ስፍራ ነው (በነገራችን ላይ አንዲት ሴት ወንዱን መውደዷን የምትገልጽበት ይህ የ“ሂዲ ደርቡ” ወግ በሀረርጌና በአርሲም ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በአርሲና በሀረርጌ “ሂዲ ደርቡ” አይባልም፡፡ እዚያ ዘንድ “አሴና” ወይንም “አሼና” እየተባለ ነው የሚጠራው፤ በተጨማሪም የሀረርጌና የአርሲ ኮረዶች ፍቅራቸውን የሚገልጹት በብዙ እምቧዮች ነው፤ ወንድዬው ጠዋት ከቤቱ ሊወጣ ሲል ሴቲቷ በአጥር ላይ ተንጠልጥላ ብዙ እምቧዮችን ከፊቱ ትበትንና ወደ ቤቷ ትነጉዳለች፤ ወንድዬውምም ጉዳዩን ለወላጆቹ ይነግርና ልጅቷን ያገባታል)፡፡

በ“ሂዲ ደርቡ” እና “በሎሚ መወርወር” መካከል ያለው ትልቁ ልዩነት ግን ከላይ ከተገለጹት ውስጥ የለም፡፡ ትልቁ ልዩነት ወዲህ ነው ያለው፡፡ እንደሚታወቀው “ሎሚ መወርወር” በወንድ የሚፈጸም ወግ ነው፡፡ ሴቲቷ ሎሚውን አትወርውርም (ምንም እንኳ ያቺ ጭራ ቀረሽ የሚሏት ዘነበች ታደሰ “ሎሚ ብወረውር” እያለች ብትዘፍንም ሴቶች ሎሚ ሲወረውሩ ታይቶም ተሰምቶም አይታወቅም)፡፡ የጅማዋ ተሚማ የምትፈጽመው “ሂዲ ደርቡ” ግን በራሷ የሚፈጸም እንጂ በወንድ የሚፈጸምላት አይደለም፡፡ ወንድዬው ፍቅሩን የሚገልጸው ነጠላ ገዝቶ በማልበስ ነው እንጂ እምቧይ በመወርወር አይደለም፡፡
ታዲያ ተሚማ የምትወደውን ሰው በእምቧይ የመምታቷን ጀብድ ስትገለጸው ሰምታችኋት ታውቃላችሁ?… ካላወቃችሁ “ፌይሩዝ” የተባለች ወጣት ያዜመችውን በትንሹ ቀንጨብ አድርገን እናሳያችሁ (ከፌይሩዝ የተዋስነው አባባል ለተሚማም ይሆናል)፡፡
Akkasumaan hiddii darbannaanii (ለዚያው ነው እምቧይ መወርወሬ)
Sijaaladhe giddiin naqbnaanii (ግድ ብሎኝ ነው አንተን አፍቅሬ)
ተሚማ! ጉብሊቷ ወጣት የጅማ!! ስትወደን እንዲህ ነው የምትለን፡፡ ለፍቅር መረታቷን እንዲህ ነው የምታስረግጠው፡፡ ፍቅሯ ሲባባስባት ደግሞ በጣፋጭ አንደበቷ እየዘማመረች ልባችንን ልታፈርሰው ትችላለች፡፡ እንዲያውም ታዋቂዋ የጅማ ተወላጅ አርቲስት ሲቲና አባዱላ “ቡርቱካኒ” ብላ ያዜመችው ዝነኛ ዘፈን ተሚማ በፍቅር በምትጨነቅበት ጊዜ የምትቀኘውን እንጉርጉሮ ሊወክል ይችላል፡፡ እስቲ ደግሞ የሲቲናን ዘፈን እንዋስና የተሚማን የፍቅር ብሶት እንግለጽ፡፡
Burtukaani mitii hadhaadha miti hadahaadha (ብርቱካን አይደለም ይህስ መራራ ነው)
Kun jaalalaa miti maraachaadha (ፍቅርስ አይደለም ይህስ እብደት ነው)
እጥር ምጥን ቅልብጭ ያለች ግጥም፡፡ የፍቅር ፍላጻ ልቧን ወግቶ ህመሙ በሚያስጨንቃት ጊዜ ነው እንዲህ ብላ የምታዜመው ተሚማ! ያቺ ውብ ቄጤማ! የአባጅፋር ልጅ የጅማ!!
*****
ብራቮ! ብራቮ! ተሚማ ሙገሳችንንና መወድሳችን ከልብ የፈለቀ መሆኑ ስለገባት በጅማ ምድር ልታንሸራሽረን የገባችውን ቃል በድጋሚ አድሳለች፡፡ በመሆኑም ጅማን ልናስሳት ነው፡፡ በአሰሳችን ድብርት ቢገጥመን ተሚማ በጣፋጭ አንደበቷ “Hin mukaayinaa” እያለች  ታባርረዋለች (Hin mukaayinaa ብዬ ስጽፍ ሳቅኩኝ….ቂቂቂቂቂቂ… ቢሆንም በጣም ደስ እያለኝ ነው የምስቀው… እንደ ሐላዋ በሚጣፍጥ አባባል ድብርትን ማባረር ይሏል ይሄ ነው… Hin mukaayinaa)
“Hin mukaayinaa” ምን ዐይነት ትርጉም እንዳለው አውቃችኋልን?…. “እንጨት አትሁኑ” ማለት እኮ ነው፡፡ ከሩቅ ሀገር ሊገበኘን የመጣ ሰው እንግድነት እንዳይሰማው ለማድረግ ከፈለግን “አትቦዝን” እንለዋን አይደል?… አዎን! በፈረንጅኛውም “Just feel at home” ለማለት ይቻላል፡፡ የጅማዋ ተሚማ ግን “Hin mukaayin” ማለትም “እንጨት አትሁን” ነው የምትለው፡፡ ተሚማ የምትጠቀምበት Hin mukaayinaa ውስጠ ወይራ ፍቺን ያዘለ ሐረግ ነው፡፡ “ማዕና”ውም እንዲህ ሊሆን ይችላል፡፡
   እንግድነት የሚሰማው ሰው ዝምታ ያበዛል፡፡ ከሰዎች መሃል የወጣ ይመስለዋል፡፡ ይህም በመንገድ ላይ ለብቻው ከቆመ ዛፍ ወይንም የኤሌክትሪክ እንጨት ጋር ያመሳስለዋል፡፡ እርሱን የተጫጫነው ስሜትም በኛ ላይ የድብርት መአት ሊጠራብን ይችላል፡፡ እንግዲህ ሰውዬው እንግድነት ተሰምቶት እንደ እንጨት ድርቅ ብሎ ድብርት እንዳይጠራብን ለማድረግ በሚል ነው ተሚማ Hin mukaayin” የምትለው፡፡ ደስ ሲል!!
Hin mukaayinaa” እንዳለችው ተሚማ እኛም “ሂንሙካይና ጋ ማሎ” እንላችኋለን!!
(ይቀጥላል)
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 22/2007
ሀረር… ምስራቅ ኢትዮጵያ
—–
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of ethnography and history with special focus on Eastern Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
 በለምለሚቷ ምድራችን ላይ እየተሽከረከረ ዚያራ ማድረግ ወጉ የሆነው የኢትኖግራፊ ፈረሳችን ታሪካዊቷን ጅማንና ህዝቧን መጎብኘት አሰኘው፡፡ እኛም “አበጀህ! ጥሩ ሀገር መርጠሃል” በማለት መረቅነው፡፡ ፈረሳችንም የደቡብ ምዕራብ አቅጣጫን ይዞ ገሰገሰ፡፡ ከጊቤ ዉሃ ከተጎነጨ በኋላም ወደ ታሪካዊቷ ቀበሌ ሰተት ብሎ ገባ፡፡
The palace of Abba Jifar, Jimma,
ጅማ! የአባጅፋር ሀገር! የአባ ፎጊ ሀገር! የአባ ቦጊቦ ሀገር! የአባ ጎመል ሀገር! ዝንተ-ዓለም አይረሴ የሆኑ ነገሥታት ታሪክ ሰርተውባት ለታሪክ ያኖሯት ውብ መንደር!!
ጂማ! የሰቃ ጨቆርሳ ሀገር! የጌራ ሀገር! የጉማ ሀገር! የጎማ ሀገር! የሊሙ ሂናሪያ ሀገር! አምስቱ የጊቤ መንግሥታት የለመለሙባት ምድር!!
ጅማ! የአባ ሚዛን ሀገር! የአባ ቆሮ ሀገር! የአባ ገንዳ ሀገር! የአባ ዱላ ሀገር! በኦሮሞ ምድር የዘመናዊ ቢሮክራሲ ጥንስስ የተጀመረባት ሰፈር!
ጅማ! የአቦል ሀገር! የበረካ ሀገር! የቃህዋ ጀባ ሀገር! ለስምንት መቶ ዓመታት ተወዳጅነቱ ሳይቀንስ የዘለቀውን “ቡና”ን ለዓለም ያበረከተች የሙሐባ መንበር!!
ጅማ! የተሚማ ሀገር! የገሜቲ ሀገር! የአያንቱ ሀገር! የአስሊያ ሀገር! የበድሪያ ሀገር! የፈይሩዝ ሀገር! ውብ ልዕልታትና ወይዛዝርት የወጡባት ምድር!!
*****
ተሚማ ነው ያልኩት! ይገርማል!! ገና የፈረሳችን ኮቴ መሬቱን ከመርገጡ ተሚማ በፈገግታ ታጅባ ልትቀበለን መጣች፡፡ ተወዳጅዋ የጅማ ጉብል!
ወይ አፈጣጠር!! “ቁርጥ ባለቤቴን” አለ ሰውዬው፡፡ በእውነት ይህቺ የጅማ ጉብል ናት ወይስ በሀረርጌ የምናውቃት ቀሽቲ?… እንዲያው ሁለመናዋ ከኛዋ ቀሽቲ ጋር አንድ ነው እኮ!!
ይህቺን “ኑረል ዐይን” የምትመስል ጉብል በተራ ሰላምታ ማነጋገር ተገቢ መስሎ አልታየንም፡፡ በመሆኑም ድሮ የ“ሐፈዝናቸውን” ሙገሳዎችና በቅርብ ጊዜያት የሰማናቸውን “ወለሎ”ዎች ተራ በተራ እየደረደርን ዐጃኢብ እስክትል ድረስ እንዘምርላታለን፡፡
*****
እውነቴን ነው!! ለጂማዋ ጉብል ማን ያልዘመረ አለ?… ብዙ ተዘፍኖላታል፡፡ ብዙ ተብሎላታል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ለርሷ የተደረደረው ሙገሳ በጣም ያንሳታል፡፡ እልፍ አዕላፍ “ቀሲዳ”፣ “ሩባኢያት”፣ “ወለሎ”፣ “ቅኔ”፣ “ገዛል”፣ ወዘተ… ይገባታል፡፡ የኛም ዚያራች ያማረ ይሆንልን ዘንድ ወደ ሌሎች ወጎች ከማለፋችን በፊት ለርሷ ክብር የተዜሙትን ዜማዎች አንዴ በጀመዓ ብንከልሳቸው መልካም ይመስለኛል (በአጸፌታው የጂማዋ  ጉብል  ደረጃውን የጠበቀ መስተንግዶ አድርጋልን ዚያራችንን ልታደምቀው ተሰናድታለች)፡፡
ለጅማዋ ጉብል የተዜመው የመጀመሪያው ዜማ የትኛው እንደሆነ በትክክል አናውቅም (አንቺ ተሚማ! ያ ገሜቲ ጂማ!! ያ በሬዱ ነማ!! እኛ “እኛ” መሆናችንን ታውቂዋለሽ አይደል?…. አዎን!  “እኛ” እያልን የምንጽፈው ከሀረርጌ በመሆናችን ነው)፡፡ እስካሁን ድረስ ባለን መረጃ መሰረት ግን የጥላሁን ገሠሠ “ሰላመካ ያ ገንኔ ሰላመካ” ለጅማዋ ጉብል የተዘፈነ የመጀመሪያው ዜማ ይመስለኛል፡፡ የግጥሙ ደራሲ ተገኑ ባልከው ይባላል (“አሸም ያ ማተቤ”ንም የጻፈው እርሱ ነው)፡፡ ጥላሁን ለጅማዋ ጉብል ሲዘፍን እንዲህ ነበር ያለው፡፡
Salaama kaa yaa gannee salaama kaa
Harka fuune yaa immeetee salaamka.
Dubbiin Tamiima dubbiin mucayyoo magaala
Ija koo qabee gurra koo qabee na raasa
Gandan dhagayee dhiisi naan jenaani
Ittin dhiise yaadden na qabnaani.
ጥላሁን በዘፈኑ ውስጥ የጅማን ስም አልጠቀሰም፡፡ ነገር ግን በግጥሙ ውስጥ የተጠቀማቸውን ቃላት እና የሙዚቃውን ምት (rhythm) በአንክሮ ስናያቸው ዘፈኑ “ለጅማዋ ተሚማ” እንደተዘፈነ በቀላሉ መረዳት እንችላለን፡፡ ለምሳሌ ከበርካታ የኦሮምኛ ዘዬዎች መካከል “ሰላመ-ካ” እያሉ ሰላምታ መስጠት የሚቻለው በጅማው ዘዬ ነው፡፡ “ሰላመት” ከዐረብኛ ወደ ኦሮምኛ የገባ ቃል መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ቃሉ በኦሮምኛ ውስጥ የሚያገለግልበት ስልት እንደየአካባቢው ይለያያል፡፡ በሀረር ኦሮምኛ አንድን ሰው ስንገናኝ “ሰላም ጄኔ” (ሰላም ብለናል) ለማለት እንችላለን፡፡ በጅማው ዘዬ ደግሞ “ሰላመ-ካ” እንላለን (ሌሎች ስልቶችን ከወደታች እንመጣባቸዋለን)፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ጥላሁን ልጅቷን “ተሚማ” እያለ ነበር የጠራት፡፡ ይህም ዘፈኑ ለጅማ ጉብል የተዜመ መሆኑን ያሳብቃል፡፡ የጅማ ሴቶች ከሚጠሩባቸው ስሞች መካከል በጣም ዝነኛ የሆነው እርሱ ነው፡፡ ሌሎች አርቲስቶችም የጅማን ኮረዳ ለመጥራት ሲፈልጉ በዚህ ስም ነው የሚጠቀሙት (ጥላሁን “ፋጡማ” ወይንም “አዒሻ” ቢል ኖሮ ለሀረር ቆንጆ ነው ያዜመው ብለን እንጠረጥር ነበር)፡፡
*****
ከጥቂት ዓመታት በፊት ነው፡፡ “ሃጫሉ ሁንዴሳ” (Haacaaluu Hundeessaa) የሚባል የኦሮምኛ ዘፋኝ መጀመሪያ ካሴቱ በሙዚቃ አፍቃሪያን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን አግኝቶ ነበር፡፡ በካሴቱ ውስጥ ከተካተቱት ዜማዎች መካከል በጣም ተወዳጅ ሆኖ የወጣው ደግሞ ለጅማዋ ጉብል የተገጠመው ነው፡፡ ሃጫሉ ከጅማ ጉብል የያዘውን ፍቅር ሲገልጽ እንዲህ ነበር ያለው፡፡
Galaanni Gibee guutus daaktuuf bidiruutu nama ceesisaa
Garaan jaalatte hin rafuu halkuu jilbibbii nama deemsisaa
Ani sossodaadhe barana qalbii kootii
Gibee gaman jaaladhe sanyii mootii.
ሃጫሉ የዘፈነውን ወደ አማርኛ ስንተረጎመው እንደሚከተለው ይሆናል፡፡
“የጊቤ ወንዝ የሞላበት ሰው በዋናተኛና በታንኳ ይሻገራል
ያፈቀረ ሆድ ግን አያስተኛም፤ ሌሊቱን በሙሉ በዳዴ ያስኬዳል፡፡
አረ ዘንድሮስ ፈራሁኝ እንዳይታመም ይሄ ቀልቤ
ከጊቤ ወዲያ ያለችውን የንጉሥ ዘር አፍቅሬ ከልቤ፡፡
ሃጫሉ የወደዳት ልጅ “ጉብል” ብቻ ሳትሆን “የንጉሥ ዘር” እንደሆነች ነግሮናል፡፡ የዚህን አባባል “ተፍሲር” ወደፊት ስለምንመጣበት በአዕምሮአችሁ ውስጥ መዝግባችሁት ቆዩ፡፡
*****
ከላይ እንደገለጽኩት ለ“ጅማ ጉብል” የተዜመው የመጀመሪያ ዜማ የጥላሁን ገሠሠ “ሰላመካ” ነው፡፡ ነገር ግን ጥላሁን “ጉብሊቷ”ን በስም አልጠቀሳትም፡፡ ታዲያ “የጅማ ጉብል” የሚለውን ሐረግ በግጥሙ ውስጥ በግልፅ (explicitly) በማሳየት ማዜሙን የጀመረው ማን እንደሆነ ታውቃላችሁን?
  ነፍሱን ይማረውና አሁን በህይወት የለም፡፡ አብደላ መሐመድ ነው፡፡ አብደላ የፖሊስ ኦርኬስትራ አባል ነበረ፡፡ በኦርኬስትራው ውስጥ በነበረው ቆይታ “አሪፍ” ጣዕመ ዜማዎችን አስመዝግቦ አልፏል፡፡ ከነርሱ ውስጥ በመጀመሪያ ደረጃ ተጠቃሽ የሆነው ደግሞ “መጋለ ቀሎ ያ በሬዱ ጅማ” የተሰኘው ዘፈን ነው፡፡ አስታወሳችሁት አይደል?… አዎን!! አብደላ ያዜመው ዜማ በጣም ተወዳጅ ከመሆኑ የተነሳ በአንድ ሰሞን የህዝብ ዘፈን እስከመሆን ደርሷል፡፡ በተለይም በቀድሞው ጊዜ የኢትዮጵያ ሬድዮ የኦሮምኛ ፕሮግራም የአብደላን ዘፈን እየደጋገመ ያጫውተው የነበረ መሆኑ ኦሮምኛ የማይሰሙ ሰዎችም ጭምር የዘፈኑን ግጥሞች እንዲሸመድዱ አስችሎአቸው ነበር፡፡ እነሆ አዝማቹን ላስታውሳችሁ ነው፡፡
Jenneen ashamaan ashamaa jenneen ashamaa
Magaala qalloo yaa bareedduu Jimmaa
የአብደላ ዘፈን መልዕክቱ እንዲህ ሊሆን ይችላል፡፡
“እንዴት ነሽ… ሰላም ነሽ ወይ” አልናት፡፡
ያቺን ጠይም ጉብል የጅማ ወጣት፡፡
አብደላ በዚህ ዘፈኑ የጅማዋን ጉብል በማወደሱ ብቻ አይደለም የሚለየው፡፡ በዘፈኑ ውስጥ የጅማ ሰዎች መታወቂያ የሆነውን  የኦሮምኛ ቃል በመጠቀም ግጥሙን ያቀናበረ በመሆኑም ጭምር ነው የሚታወሰው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡
በርግጥም የጅማ ሰዎች ሰላምታ ሲሰጣጡ ከላይ በጠቀስኩት “ሰላመ-ካ” የተሰኘ ቃል ይገለገላሉ፡፡ ሆኖም ጅማዎች ሰላምታውን በመጠይቃዊ ዘዴ ሲያቀርቡልን ብዙሃኑ የኦሮምኛ ተናጋሪዎች በሚናገሩበት ስልት “አከም” (Akkam) አይሉም፡፡ ከዚህ በተለየ ስልት “አሸም” (Asham) ወይንም “አሸማ” (Ashamaa) ነው የሚሉት፡፡ አንድ ኦሮሞ የትም ሆኖ “አሸም” ብሎ ሰላምታ ካቀረበላችሁ ትውልዱ ከወደ ጅማ እንደሆነ ልብ በሉ፡፡(በነገራችን ላይ ለየት ያለ መጠይቃዊ የሰላምታ ማቅረቢያ ቃል የምናገኝበት ሌላው የኦሮምኛ ዘዬ በኢሉባቦር የሚነገረው ነው፤ የኢሉባቦር ሰዎች “አከም” ለማለት ሲሹ “አተም” ነው የሚሉት፡፡ የወለጋና የምዕራብ ሸዋ ኦሮሞዎችም  “አተም”ን ያውቁታል፡፡ ነገር ግን ወለጋዎችና ሸዋዎች በአብዛኛው “አከም”ን ነው የሚጠቀሙት)፡፡
የጅማ ሰዎች በሚያዜሟቸው ዘፈኖች ላይ በብዛት የሚጠቀሙት ሌላ ቃል አለ፡፡ እንዲያውም ያ ቃል ከቋንቋነትም አልፎ የጅማን ዘፈን የምንለይበት ምልክት (mark) እስከመሆንም ደርሷል፡፡ ለምሳሌ አንድ አርቲስት በዘፈኑ ውስጥ “አራዳ… አራዳ ሆዬ” የሚል ሐረግ ከደጋገመ ዘፋኙ ስለአዲስ አበባ እየዜመ መሆኑን በቀላሉ መረዳት እንችላለን፡፡ “እሪኩም” እና “መጋሎ” የተሰኙ ቃላትን የሚያበዛ ዘፋኝም ስለወሎ የሚያዜም ነው፡፡ ስለጅማ የሚያዜም ሰው ደግሞ ብዙ ጊዜ “አህላን አህላ” እያለ ነው ዘፈኑን የሚጀምረው፡፡
አዎን! በኦሮምኛ ጨዋታዎች ውስጥ “አህላን አህለ” ከተባለ ዘፈኑ የጅማ መሆኑ ምንም አያከራክርም፡፡ “አህለን” በመሰረቱ የዐረብኛ ቃል ነው፡፡ በዐረብኛ “አህለን ወሳህለን” ከተባለ “ጤና ይስጥልኝ” እንደማለት ነው (አገባቡ ሰፋ ሲል ደግሞ “እንኳን ደህና መጡ” እንደማለትም ይሆናል)፡፡ በሃይማኖታቸው ሙስሊሞች የሆኑት የጅማ ሰዎች “አህለን”ን ከዐረብኛ ወርሰው ነው ቤተኛ ያደረጉት፡፡
*****
ጅማዎች “አህለ”ን የሚሉት ከልብ የመነጨ ስሜታቸውን ለመግለጽ ነው፡፡ እኛ ጅማ ስንገባ የፈረሳችንን ልጓም ይዛ የጅማን መሬት እንድንረግጥ የረዳችን “ተሚማ”ም ከፈገግታ ጋር “አህለን” በማለት ተቀብላናለች፡፡ እንግዲህ በርሷ አስጎብኚነት “አህለን አህለን” አያልን በጅማ መሬት መንሸራሸራችንን ልንጀምር ነው፡፡
አህለን አህላ… ሸጌ አህለን አህላ
አህለን.. አህላ.. ጊፍቲ አህለን አህላ
(ይቀጥላል)
—–
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 22/2007
ሀረር… ምስራቅ ኢትዮጵያ
—–
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of ethnography and history with special focus on Eastern Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.


ፀሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
——
የልጅ እያሱ ሞት ይፋ የወጣው በህዳር ወር 1928 ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ወደ ማይጨው ከመዝመታቸው ሶስት ቀን አስቀድሞ ነው። በአሟሟታቸው ዙሪያ ከሚነገሩት መካከል
·        ልጅ እያሱ የተገደሉት ሀረር ውስጥ ነው::
·        ልጅ እያሱ የተገደሉት አዲስ አበባ ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ውስጥ ሲሆን የተቀበሩትም ከቤተ መንግሥቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከሚገኘው ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ክልል ነው::
·        ልጅ እያሱ የቀብራቸው ስነ-ስርዓት የተከናወነው ደብረ ሊባኖስ ነው::
·        ልጅ እያሱ የተቀበሩት ሰንዳፋ ውስጥ ነው የሚሉት ይገኙባቸዋል።
የልጅ እያሱን አሟሟት አውቃለሁ በማለት እማኝነታቸውን ከሰጡ ግለሰቦች መካከል አገልጋያቸው የነበሩ አዛውንት ኢጣሊያኖች አቤቶ እያሱን ከጋራሙለታ እስር ቤት ለማስወጣት ሙከራ አድርገው እንደነበር በመግለጽ እንዲህ ይላሉ።
 
 “የኢጣሊያ ወኪሎች አባጤናን ከግራዋ እስር ቤት ለማስወጣት ከሞከሩ ጀምሮ ልዑልነታቸው በእስር ቤቱ ክልል እየተከዙ ወዲያ ወዲህ ይንጎራደዱ ነበር። አንድ ቀን ምሽት አንዲት አውቶሞቢል ወደ እስር ቤቱ መጣች። እርሳቸውም ይፈሩት የነበረው ሰው መኖር አለመኖሩን ጠየቁ። በቀጣዩ ቀን “የመጡት አባ ሐና ብቻ ናቸው” አልኳቸው። ነገር ግን ጥቂት ዘግይቶ ሁለተኛዋ አውቶሞቢል ሁለት ሰዎችን አሳፍራ መጣች። ከሁለቱ አንዱ ፊታውራሪ ነበር። እስኪጨልም ቆይተው እያደቡ ወደ እስር ቤቱ ተጠጉ። መዝጊያው ሰፋፊ ስንጥቆች ያሉት በመሆኑ ልዑልነታቸው በስንጥቆቹ ውስጥ አዘውትረው ምራቃቸውን ጢቅ ይሉ ስለነበር ሲያነጣጥሩባቸው ሳያዩአቸው አልቀረም። በተኮሱባቸው ጊዜ የመስኮቱን መቃኖች ጨምድደው ጨበጡ። ኃይለኛ ስለነበሩ ቤቱን በሙሉ ያናጉትና የሚናድ መስሎኝ ፈርቼ ነበር። ተንገዳግደው ወለሉ ላይ ሲወድቁ ሰማሁ። ሬሳቸው በባቡር ተጭኖ ወደ አዲስ አበባ ከመወሰዱ በፊት ሁለቱ ነፍስ ገዳዮች እንደ ባላዛር ሬሳቸው ላይ ተጎንብሰው አጓሩ። ሬሳቸው አዲስ አበባ እንደደረሰ ከፍተኛ ባለስልጣን ለባላምባራስ አበበ አረጋይ አስረከቡ። እንግዲህ ሬሳቸው ለዘላለም ያረፈበትን ቦታ የሚያውቁት ባላምባራስ አበበ አረጋይ ብቻ ናቸው። ይሁንና እኒሁ ሰው ደግሞ በ1953 በተሞከረው የመንግሥት ግልበጣ ጊዜ የመከላከያ ሚኒስትር ሆነው ነበርና በአረንጓዴው የገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ታዛ ወለል ላይ ደማቸው ፈስሶ ሞቱ። አባ ሃና ጂማም ተመሳሳይ እጣ ገጠማቸው”።
    እንደ አዛውንቱ ምስክርነት ከሆነ አባ ሐና ጅማም ሆነ አበበ አረጋይ የልጅ እያሱን አስከሬን በተረካከቡበት ቦታ ላይ ስለተገደሉ ምስጢሩ አብሮ ሞቷል ማለት ነው።
ሌላኛዋ ለቤተ መንግሥቱ ቅርበት ያላቸው ሴት ደግሞ ለጎበዜ ጣፈጠ እንዲህ ብለው ነበር የተናገሩት (“አባ ጤና እያሱ” ከተሰኘው የጎበዜ ጣፈጠ ድርሰት የተወሰደ ነው)።
    “ዕለቱን አላስታውስም። ቢሆንም ልጅ እያሱ አርፈዋልና ቤተ መንግሥት እንድትመጡ የሚል መልዕክት ተላለፈ። እኛም ማልደን ወደ ቤተ መንግሥቱ ሄድን። አዲስ አበባ ውስጥ የምንገኝ ወይዛዝርትና መኳንንት ተሰብስበን ስንላቀስ ዋልን። ሬሳ ግን አልነበረም። እቴጌ መነን በጣም አዝነውና ተክዘው እንባቸውን ያፈሱ ነበር።  ጃንሆይ በርኖሳቸውን ገልብጠው ደርበው ወንድሜ ወንድሜ በማለት ያለቅሱ ነበር።”
ልጅ እያሱን በታሸገ ባቡር አሳፍሬ ወደ አዲስ አበባ ልኬአቸኋለሁ በማለት እማኝነታቸውን የሚሰጡት ብላቴን ጌታ ዶ/ር ሎሬንዞ ታዕዛዝ በበኩላቸው የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን ቄስ የነበሩ ገ/መድህን የተባሉ ግለሰብ እንዲህ በማለት ነግረውኛል ይላሉ።
“በቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን ትይዩ የዱክ ቤት ይባል በነበረው ህንጻ ሰገነት ላይ አንድ እጆቹን በሰንሰለት የታበተ ሰው ከቀትር በኋላ ዘወትር ሲመላለስ እናየው ነበር። ነገር ግን ጃንሆይ ወደ ጦርነቱ ከመዝመታቸው በፊት ሌሊቱን ጸሎተ ፍትሐት እንድናደርግ ታዘዝን። ሆኖም የሟቹን ሰው የክርስትና ስም የሚነግረን አልነበረም። ከዚያ በኋላ ያ ሰውዬ ይመላለስበት ከነበረው ሰገነት ላይ አልታየም። እኛም የሞቱት ልጅ እያሱ እንደሆኑ ተረዳን።
(ምንጭ፡- ጎህ መጽሄት፣ ቅጽ 1 ቁጥር 5፣ ጥቅምት 1993፣ ገጽ 6/22)
—————–
ለዚሁ መጽሄት ቃለ-ምልልስ የሰጡት የልጅ እያሱ የልጅ ልጅ ፕሮፌሰር ግርማ ዮሐንስ እያሱ ቄስ ገ/መድሕን የተባሉት ሰው ከሰጡት ምስክርነት ጋር የሚጣጣም ቃል አሰምተዋል። ፕሮፌሰር ግርማ እንዳሉት ልጅ እያሱ በስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ባለው የዱክ ቤት (አሁን Law Faculty ዋና ህንጻ የሆነው) መታሰራቸው እውነት ነው። “አጼ ኃይለ ስላሴ ወደ ማይጨው ሀሙስ ከመዝመታቸው በፊት ማክሰኞ ሌሊት ልጅ እያሱ ተገድለው አሁን የዩኒቨርሲቲው የእግር ኳስ ሜዳ ከሆነውና ያኔ የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን አጸድ ከነበረው ስፍራ ተቀብረዋል” ይላሉ ፕሮፌሰር ግርማ።
—————
አፈንዲ ሙተቂ
ሰኔ 22/2005
ሀረር- ምስራቅ ኢትዮጵያ


ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
===ለመግቢያ ያህል====
    “የትግል ስም” ቃሉ እንደሚያመለክተው በትግል ዓለም ውስጥ ላለ ሰው ነው የሚያገለግለው፡፡ ታጋዩ በትግል ዓለም ውስጥ እያለ የሚጠቀምበት መጠሪያው ነው፡፡ ታጋዮች የትግል ስምን የሚጠቀሙት በልዩ ልዩ ምክንያቶች ነው፡፡ ዋነኛው ምክንያት ግን ታጋዩ በእውነተኛ ስም ሲጠቀም ሊደርስበት ከሚችል አደጋ ለመከላከል የሚል ነው፡፡
     
የትግል ስም እንደ ብዕር ስም በሚስጢራዊነት አይያዝም፤ ሰውዬው ድሮ የሚታወቅበትን ስም ተክቶ በስራ ላይ የሚውል ነው፡፡ ታጋዩ ወደ ትግል ዓለም ከገባ በኋላ የሚያገኛቸው የትግል ጓዶች በትግል ስሙ ነው የሚጠሩት፡፡ በመታወቂያም ሆነ በሌሎች ሰነዶች ጥቅም ላይ የሚውለውም የትግል ስም ነው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ ትግሉን በድል ካጠናቀቀ በኋላም በአብዛኛው በትግል ስሙ መገልገሉን ሲቀጥልበት ይታያል፡፡
   የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅም ላይ ያለው ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ ሆኖም የሩሲያ ኮሚኒስቶች በትግል ስም በብዛት በመጠቀም ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ እንደ ቭላድሚር ሌኒን፣ ጆሴፍ ስታሊን፣ ሊኦን ትሮትስኪ፣ ሉሊ ማርቶቭ ያሉ ስሞች በሙሉ የትግል ስሞች ናቸው፡፡ በሌሎች ሀገሮች የነበሩ ኮሚኒስቶችም በትግል ስም በብዛት ይጠቀሙ ነበር፡፡ ሆ ቺ ሚን፣ ኪም ኢል ሱንግ፣ ቼ ጉቬራ የመሳሰሉ መጠሪያዎች የትግል ስሞች ናቸው (የቼ ጉቬራ ትክክለኛ ስም “ኧርነስቶ ጉቬራ” ነው፤ የኪም ኢል ሱንግ ትክክለኛ ስም “ኪም ሱንግ ቹ” ነው)፡፡
====የትግል ስም በኢትዮጵያ===
   የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በስራ ላይ ያዋለው ኢትዮጵያዊ ማን እንደሆነ በትክክል አይታወቅም፡፡ ሆኖም ከተማሪዎች ንቅናቄ የፈለቁት ወጣቶች የፋኖነት ህይወት በጀመሩበት ዘመን በብዛት ስራ ላይ እንደዋሉት ይታወቃል፡፡ ታዲያ እነዚያ ፋኖዎች የትግል ስምን የሚጠቀሙበት ምክንያትና ስሙን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዘይቤ አንድ ወጥ አልነበረም፡፡ በህቡዕ እና በትጥቅ ትግል መንግሥትን ለመለወጥ የሚታገሉ ድርጅቶች ከተመሰረቱ በኋላ በጣም ጎልብቶ የመጣው የትግል ስም አጠቃቀም ልማድም እንደ ፓርቲው ይለያያል፡፡ ከዚህ በማስከተልም በቀደምት ድርጅቶች ውስጥ ይሰራበት የነበረውን ልማድ በአጭሩ እናወሳለን፡፡
1.      ጀብሃ እና ሻዕቢያ
ጀብሃ እና ሻዕቢያ የትግል ስምን የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ አልተመዘገበም (ወይም አላነበብኩም)፡፡ ሆኖም ሁለቱም ፓርቲዎች የሚስጢር ስም የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ በስፋት ይታወቃል፡፡ በተለይም ታጋዮቹ ለየት ያለ ተልዕኮ በሚፈጽሙበት ወቅት በሚስጢር ስም እንዲጠቀሙ ይደረጋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጀብሃና ሻዕቢያ ዘንድ ታጋዩን በቅጽል ስም መጥራት በጣም የተለመደ ነው፡፡ ለምሳሌ የጀብሃው “መሐመድ ቺክኒ”፣ የሻዕቢያዎቹ “ወልደ ዲንክል”፣ “ተክላይ አደን”፣ “ሀይሌ ጀብሀ” ይጠቀሳሉ፡፡ “የማነ ጃማይካ” የሚባለው የህወሐት ታጋይም ከድሮ የሻዕቢያ አባል በነበረበት ዘመን ሲጠራበት በነበረው ቅጽል ነው የሚታወቀው፡፡   
2.     ህወሐት
ህወሐት በትግል ስም የመጠቀም ሰፊ ልማድ አለው፡፡ በትጥቅ ትግሉ ዘመን ፓርቲው እያንዳንዱ ታጋይ በትግል ስም እንዲጠቀም ያደርግ ነበር፡፡ እነዚያ ታጋዮች ከትጥቅ ትግሉ ፍጻሜ በኋላም በትግል ስማቸው መጠራታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በዚህ ረገድ ከፓርቲው የተገለሉትም ሆነ በፓርቲው ውስጥ ያሉት ተመሳሳይ መንገድ እየተከተሉ ነው፡፡
ህወሐቶች የትግል ስም የሚመርጡት ስማቸውን ሙሉ በሙሉ በመቀየር አይደለም፡፡ የታጋዩ የልደት ስም ብቻ ነው የሚለወጠው እንጂ የአባቱ ስም አይቀየርም፡፡ ከታዋቂ የህወሐት ሰዎች መካከል የሚከተሉትን ከትግል ስማቸው ጋር መጥቀስ ይቻላል፡፡
1.      እምባዬ መስፍን= ስዩም መስፍን
2.     ዘርዑ ገሠሠ= አግዓዚ ገሠሠ
3.     መሐሪ ተኽለ= ሙሴ ተኽለ
4.     አምሀ ጸሐየ= አባይ ፀሐየ
5.     ዮሐንስ ገ/መድህን= ዋልታ ገ/መድህን
6.     ስዕለ አብርሃ= ስዬ አብርሃ
7.     ወልደስላሤ ነጋ= ስብሐት ነጋ
8.     ለገሰ ዜናዊ= መለስ ዜናዊ
9.     ራስወርቅ ቀጸላ= አታኽልቲ ቀፀላ
10.    ገሰሰው አየለ= ስሁል አየለ
11.     መሐመድ ዩኑስ= ሳሞራ ዩኑስ
12.    ዮሐንስ እቁባይ= አርከበ እቁባይ
13.    ሐዱሽ አርኣያ= ሀየሎም አርኣያ
    ህወሐቶችም እንደ ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን በቅጽል ስም የመጥራት ልማድም አላቸው፡፡ ለምሳሌ ከህወሐት ታጋዮች የሚበዙት ሙሉጌታ ገ/ህይወትን “ጫልቱ”፣ ሰለሞን ተስፋዬን “ጢሞ”፣ ጄኔራል አበበ ተክለ ሀይማኖትን “ጀቤ”፣ ጄኔራል አብርሃ ወልደማሪያምን “ኳርተር”፣ ካሳ ገብረመድህንን “ሸሪፎ”፣ አብረሃ ታደሰን “መጅሙእ”፣ ጸጋይ በርሄን “ሀለቃ”፣ ጄኔራል ታደሰ በርሄን “ጋውና” እያሉ ነው የሚጠሩት፡፡ ግንቦት 20/1983 ከአዲስ አበባ ሬድዮ ጣቢያ “የዘመናት የህዝብ ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሰራዊት…” በማለት ያወጀውን ታጋይ በእውነተኛ ስሙ የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው፡፡ የታጋዩ ቅጽል ስም “ላውንቸር” ስለመሆኑ ግን ብዙዎቻችን እናውቃለን፡፡
 
    ከዚህ በተጨማሪ ህወሐትና ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን “ወዲ እገሌ” (የእገሌ ልጅ) እያሉ በሰሜኑ የሀገራችን ስም በሚሰራበት ባህላዊ ዘይቤ መጥራትን ያዘወትራሉ፡፡ በኦፊሴላዊ ደብዳቤዎች ጭምር “ወዲ እገሌ” የሚለውን ልማድ ሲጠቀሙ ይስተዋላል (በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ይፋ የሆኑትን የአቶ ኢሳያስና የአቶ መለስን ደብዳቤዎች አስታውሷቸው)፡፡
3.     መኢሶን
የመኢሶን ሰዎች በትግል ላይ በነበሩበት ወቅት በልደት ስማቸው ነው የሚጠቀሙት፡፡ ሆኖም ከዋነኛ ስማቸው በተጨማሪ በሚስጢር ስምም ይገለገሉ እንደነበር ከልዩ ልዩ ሰነዶች የተገኘው መረጃ ያረጋግጣል፡፡ በዚህ መሰረት የመኢሶን መስራቾች ከሚታወቁበት የሚስጢር ስሞች የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡
a.     ሀይሌ ፊዳ= መላኩ
b.     ነገደ ጎበዜ= ነጋልኝ
c.     አብዱላሂ ዩሱፍ= አደም
d.     አንዳርጋቸው አሰግድ= ወልዴ
e.     ፍቅሬ መርዕድ= ሳሙኤል
f.      ከበደ መንገሻ= ነጋ
g.     ሲሳይ ታከለ= አሸናፊ
h.     ንግስት አዳነ= አይዳ
i.      ተረፈ ወልደጻዲቅ= ሚካኤል
ታዲያ እነዚህ ስሞች ሚስጢራዊ ደብዳቤ በሚጻፍበት ወቅት ወይም ሚስጢራዊ ስብሰባ በሚካሄድበት ጊዜ ብቻ ነው የሚያገለግሉት፡፡ መኢሶኖች በመታወቂያም ሆነ በፓስፖርት የሚገለገሉት በዋነኛ ስማቸው ነው እንጂ በሚስጢር ስም አይደለም፡፡
4.     ኢህአፓ
ኢህአፓዎችም በትግል ላይ ሳሉ ዋነኛ ስማቸውን በመተው በፓርቲው በሚሰጣቸው ስም ይገለገሉ ነበር፡፡ ፓርቲውን ወክለው በሚገኙበት መድረክ ሁሉ በዚያው ስም ነበር የሚጠቀሙት፡፡ ለታጋዮቹ የትግል ስም የሚሰጥበት ዘይቤ ግን አንድ ወጥ አይደለም፡፡ አንዳንድ ታጋዮች የልደት ስማቸውን ብቻ ይለውጡና ሌላ ቅጥያ ሳያስከትሉበት በዚያው ይጠራሉ (ለምሳሌ “ጋይም” እና “አያልነሽ”ን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ አንዳንዶች ግን የአባታቸውን ስም ጭምር ይለውጣሉ፡፡ ከዚህ ሌላም ብዙዎቹ የኢህአፓ ታጋዮች ከትግሉ ዓለም ከተገለሉ በኋላ ወደ ቀድሞ ስማቸው ሲመለሱ ይታያል፡፡ ከኢህአፓ አባላት የትግል ስሞች የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
a.     ክፍሉ ታደሰ= ታዬ አስራት
b.     መላኩ ተገኝ= ያፌት
c.     ገብረ እግዚአብሄር ወልደሚካኤል= ጋይም
d.     የዓለም ገዥ ከበደ= አያልነሽ
e.     መርሻ ዮሴፍ= በላይነህ ንጋቱ
  
በነገራችን ላይ ድሮ የኢህአፓ ታጋዮች የነበሩት የአሁኖቹ የኢህዴን/ብአዴን ዋነኛ ባለስልጣናት በትግል ስማቸው ነው የሚጠሩት፡፡ እንደምሳሌም መብራቱ ገ/ህይወት (በረከት ስምኦን)እና ፍቅሩ ዮሴፍን (ህላዌ ዮሴፍ) መጥቀስ ይቻላል፡፡ ጌታቸው ጀቤሳ በበኩሉ ለረጅም ጊዜ በትግል ስሙ ሲጠቀም ከቆየ በኋላ ከኢህዴን ሲወጣ “ያሬድ ጥበቡ” የተሰኘውን እውነተኛ ስሙን መጠቀምን መርጧል፡፡
5.     ኦነግ
 
 ከላይ የጠቀስኳቸው ድርጅቶች የትግል ስምን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዋነኛ ምክንያት የታጋዮቻቸውንና ደህንነት ለማስጠበቅ በሚል ነው፡፡ በተለይም ታጋዩ በተወለደበት አካባቢ ለውጊያም ሆነ ለሌላ ተልዕኮ የሚሰማራ ከሆነ በዋነኛ ስሙ ቢጠቀም ህይወቱ አደጋ ላይ ይወድቃል ተብሎ ስለሚታመን ነው በትግል ስም እንዲጠቀም ሲደረግ የነበረው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ በትግል ስም ቢጠቀም በወላጆቹና በሌሎች ዘመዶቹ ላይ አደጋ እንዳይደርስባቸው ለመከላከል ይረዳል የሚል ምክንያት ከድርጅቶቹ ይቀርብ ነበር፡፡
    የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ባህል ግን ከዚህ ይለያል፡፡ በዚህ ድርጅት ውስጥ ያለ ታጋይ የትግል ስም እንዲጠቀም የሚደረገው በዋነኛነት ለታጋዩ ደህንነት ተብሎ አይደለም፡፡ ከታጋዩ ደህንነት በላይ ለድርጅቱ አንድነት ጠቃሚ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ የኦነግ ሰዎች ታጋዮቻቸው በትግል ስማቸው ቢጠቀሙ ሀይማኖትና ክፍለ ሀገርን አስታክኮ የሚመጣ መከፋፈልን ለመከላከል ይረዳል በማለት ያምናሉ፡፡ አንድ ታጋይ በስሙ ብቻ ተለይቶ ጥቃት እንዳይደርስበት ለመታደግም ጠቃሚ ነው በማለት ያስረዳሉ፡፡ 
     በዚህም መሰረት የኦሮሞ ስም የሌለው ታጋይ (አሕመድ፣ አብደላ፣ አበበ፣ ከበደ ወዘተ… በመሳሰሉት የሚጠራ) ወደ ድርጅቱ ሲመጣ ቀዳሚ ስሙን ይተውና በኦሮሞ ስም እንዲጠራ ይደረጋል፡፡ የታጋዩ የአባት ስም ኦሮምኛ ካልሆነ እርሱንም ይቀይራል፡፡ ታዲያ ታጋዩ የአባቱን ስም የሚመርጠው በዘፈቀደ አይደለም፡፡ የዘረግ ሀረጉን ወደላይ ሲቆጥር መጀመሪያ የሚመጣበትን የኦሮሞ ስም (የኦሮሞ ስም ያለው ቅመ-አያት የሚጠራበትን) ነው እንደ አባቱ ስም የሚገለገልበት፡፡ የአባቱ ስም ኦሮምኛ ከሆነ (ለምሳሌ እንደ ዮሐንስ ለታ) የራሱን ስም ብቻ ነው የሚቀይረው፡፡ ታጋዩ ይዞት የመጣው ሰው ሙሉ በሙሉ ኦሮምኛ ከሆነ ግን በስሙ ላይ የሚደረግ ለውጥ የለም (እንደ ምሳሌም ባሮ ቱምሳ፣ ኢብሳ ጉተማ፣ አባቢያ አባጆብር የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ ሆኖም ጥቂት የኦነግ ሰዎች ይህንን ልማድ አልተከተሉም፡፡ ከዚህ አሰራር ጋር በማይጣጣም መንገድ ነው የትግል ስማቸውን የመረጡት፡፡ እንደ ምሳሌም በተከታታይ የኦነግ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡትን በሪሶ ዋቤ፣ ገላሳ ዲልቦ እና ዳውድ ኢብሳን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ድርጅቱን ከውጪ ሀገር የተቀላቀሉትም እንደ አዲስ የትግል ስም ሲሰጣቸው አይታይም (ለምሳሌ ጣሃ አብዲ፣ በያን አሶባ ወዘተ.. ይጠቀሳሉ)፡፡ ከታዋቂ የኦነግ ሰዎች መካከል የጥቂቶቹ የትግል ስም እንደሚከተለው ነው፡፡
a.     አብዱልከሪም ኢብራሂም= ጃራ አባገዳ (ከኦነግ በልዩነት ወጥቶ “የኦሮሞ ነጻነት እስላማዊ ግንባር” የተሰኘውን ድርጅት ቢመሰርትም ከኦነግ መስራቾችም አንዱ ነበር)
b.     መገርሳ በሪ= በሪሶ ዋቤ
c.     ዮሐንስ በንቲ= ገላሳ ዲልቦ
d.     ፍሬው ኢብሳ= ዳውድ ኢብሳ
e.     ቃሲም ሑሴን= ነዲ ገመዳ
f.      ዮሐንስ ለታ= ሌንጮ ለታ
g.     አብረሃም ለታ= አባጫላ ለታ
h.     ዮሐንስ ኖጎ= ዲማ ኖጎ
i.      አብዱልፈታህ ሙሳ= ቡልቱም ቢዮ
j.      ጀማል ሮበሌ= ጉተማ ሀዋስ
————-
መጋቢት 28/2006
አፈንዲ ሙተቂ


 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
አንጋፋውን ሱዳናዊ ድምጻዊ ዐብዱልከሪም አል-ካብሊን ከዚህ ቀደም ተዋውቀነው ነበር፡፡ ታዲያ የዚህን ጎምቱ ሰው ድምጽ ዛሬ ከአንድ ጓደኛዬ “አይፓድ” ውስጥ ሰማሁትና በሃሳብ ወደ ልጅነቴ ወሰደኝ፡፡ እናም ከርሱ ጋር “ሸዛ ዛሂር” እያልኩ ሳንጎራጎር “ስለዚህ ዘፈን ለምን አንድ ነገር አልጽፍም?” የሚል ሃሳብ መጣብኝ፡፡ እነሆ ጻፍኩላችሁ!!
*****

Abdul-Keriem Al-Kabli, the legendary Sudanese music icon.

አል-ካብሊ ከሌሎች ሱዳናዊያን ድምጻዊያን ከሚለይባቸው ባህሪዎች አንዱ አብዛኛውን ጊዜ ሙዚቃዎቹን በራሱ የሚጽፋቸው መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሙዚቃዎቹ ውስጥ ከሱዳን የዐረብኛ ዘይቤ ይልቅ ብዙ ጊዜ የጥንቱን “ዐረቢያ አልፉስሓ” (Classical Arabic) የሚጠቀም መሆኑ ነው፡፡ ሦሥተኛው ደግሞ ግጥሞቹን በሚጽፈበት ጊዜ ጥንታዊ የሆኑትን “ቀሲዳ”፣ “ቡርዳ” እና “ሙዓለቃት” የሚባሉት የዐረብኛ የስነ-ግጥም ዘይቤዎችን የሚጠቀም መሆኑ ነው፡፡
ከአል-ካብሊ ዘፈኖች መካከል በጣም የሚደነቀው “ሸዛ ዛሂር” ይባላል፡፡ “ሸዛ ዛሂር” የሚደነቀው በጥንቱ ዐረቢያ ፉስሓ የተገጠመ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን ዜማውም በጣም ማራኪ በመሆኑ ነው፡፡ የዘፈኑ አዝማች በኢራኖቹ “ሩባኢያት” ስልት የተጻፈ ሲሆን ተከታዮቹ ግጥሞች ግን በዐረብኛው “ሙዓለቃት” ስልት ነው የተጻፉት፡፡
 *****
“ሸዛ ዛሂር” በጣም የተደነቀው ግን በግጥሞቹ ውበት ሳይሆን በመልእክቱ እና ደራሲው ግጥሙን ሲጽፍ በተከተለው ለየት ያለ ተምሳሌታዊ (allegorical) ዘይቤ ነው፡፡ ግጥሙ ሲጀምር “ሸዛ ዛሂር” ይላል፡፡ “አበባው ፈነዳ… መዓዛው ምድሩን ሞላ” እንደማለት ነው፡፡ ታዲያ በዘፈኑ ውስጥ በአበባ የሚያስመስለው ሰው ሴት ሳትሆን ወንድ ነው፡፡ ወንድን አበባ እያሉ ማሞገስ አለ እንዴ?… በሌላ ቦታ አይታወቅም፡፡ አል-ካብሊ ግን አደረገው፡፡
   አል-ካብሊ የወደደውን ወንድ ሲያሞግስ “ወአንዙሩ ላ አራ በድረን አንተ ለይለተል በድሩ” ይለዋል፡፡ “ወደ ሰማይ ሳንጋጥጥ ሙሉውን ጨረቃ ለማለት አልቻልኩም፤ ምክንያቱም ያንተ ብርሃን ጨረቃውን አጨልሞታል” እንደማለት ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ “አንተ ረሒቁን ለና” እስከማለት ደርሷል (“አንተ የኛ Nectar ነህ” እንደማለት ነው፤ Nectar ወፎችና ንቦች የሚቀስሙት የአበባ ጣፋጬ ክፍል ነው፤ በአማርኛ ምን ይባላል)፡፡
አል-ካብሊ ከዚህም ርቆ ይሄድና የወደደውን ሰውዬ “ለደቱ አል-ኸምረ ዐን ሸፈቲ፤ ለዐለ ጀማለከል ኸምሩ” ይለዋል፡፡ “አንድም የመጠጥ ብርጭቆ ወደ ከንፈሬ አላስጠጋሁም፤ ነገር ግን ውበትህ “ኸምር” ሆኖ አስክሮኛል” ማለቱ ነው፡፡ ለመሆኑ ሰውዬው ምን ነክቶት ነው ወንድን እንዲህ የሚያሞግሰው (አንዳንዱ ሰው ምናልባት… Gay ሳይሆን አይቀርም ይል ይሆናል….ቂቂቂቂ)
የሰውዬውን ማንነት ከኋላ ትመጡበታላችሁ፡፡ አሁን የዘፈኑን ግጥም ተመልከቱ፡፡
(አዝማች)
ሸዛ ዛህሪን ወላ-ዛህሩ
ፈዐይነ ዚሉ ወን-ነህሩ
ረቢዑ ሪያዲና ወላህ
አሚን አህ ፊከ አን-ነሽሩ
—–
ወሐዘ ነሁሩ የብሱሙሊ ዐኒ-ድ-ዱንያ ወየፍተሩ
ወአንዙሩ ላ አራ በድረን አአንተ ለይለተል በድሩ፡፡
—–
ወቢሂ ሱክሩን ተመለከኒ ወዐጀቡን ከይፈ ቢሂ ሱክሩ
ረድቱ አል-ከእሳ ዐን ሸፈቲ ለዐለ ጀማለከል ኸምሩ፡፡
—-
ነዐም አንተ ረሒቁን ለና ወአንተ ሲሕሩ ወልኢጥሩ
ወአንተ ሲሕሩ ሙቅተዲረን ወገይረል ሀይ ወሀዋ ሲሕሩ፡፡
ኹዙ ዱኒያ ቢዐጅማኢሀ ሐቢቡን ዋሒዱን ዙኽሩ
ኢዛ ጃአት መጣሊኡሁ ፈኩሉ ሰማኡና በድሩ፡፡
ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያዋቱና ኩስሩ፡፡
ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያቱና ኩስሩ፡፡
*****
የአል-ካብሊ ግጥም ቅኔያዊ ፍቺ በመጨረሻው ስንኝ ላይ ነው የሚገኘው፡፡ “ኹዙ ዱኒያኩሙ ሃዚሂ ፈዱኒያቱና ኩስሩ” ማለት “ዱኒያ ይህቺ ናትና እዩዋት፤ መጨረሻ ላይ ተሰባሪ ናት” ማለት ነው፡፡ እውነትም ዱኒያ ተሰባሪ ናት፡፡ አል-ካብሊ ግን ሰውዬን አድንቆት ሲያበቃ “ዱኒያ ተሰባሪ ናት ብሎ” ዘጋው፡፡ ከፊት የተናገረውን መቃረን ይሆናል አይደል…?
ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ አል-ካብሊ እንዲህ ያደነቀው ሰው ጓደኛው ነበረ፡፡ ይህ ጓደኛው ገጣሚ ሲሆን በጣም ውብ የሆኑ ግጥሞችን በመጻፍ ይታወቃል፡፡ አንድ ቀን ግን ሳይጠበቅ “ጭጭ” አለ፡፡ ምንም ሳይታመም ነፍሲያው ወጣች፡፡ አል-ካብሊ በዚህ ድንገተኛ አደጋ ተደናገጠ፡፡ ልቡ ተሰበረች፡፡
ጓደኛው ከተቀበረ ከጥቂት ቀናት በኋላ በሐዘኑ የተጎዳው አል-ካብሊ በምሽት ከቤቱ ወጥቶ ሰማይ ሰማዩን ማየት ጀመረ፡፡ ሰማዩን እያየ ሟች ጓደኛውን ሲያስታውስ ይህ ግጥም መጣለት፡፡ ወዲያውኑ “ሸዛ ዛሂር”ን ጻፈውና መጫወት ጀመረ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ በአንድ አልበም ውስጥ አካተተው፡፡ ግጥሙ በሱዳኖች ዘንድ ሲሰማ ዐጂብ ተባለ፡፡ የሙዚቃ ገምጋሚዎች በበኩላቸው የአል-ካብሊ የምንጊዜም ምርጥ ዘፈን በማለት ሰየሙት፡፡
*****
አል-ካብሊ “ሸዛ ዛህር”ን ከጻፈው በኋላ እንደ መግቢያ የሚጠቀምበት አጭር እንጉርጉሮም አክሎለታል፡፡ ዘፈኑ ለገጣሚው ጓደኛው የተጻፈ መሆኑን በግልጽ የሚያሳውቀው በዚህ እንጉርጉሮ ውስጥ ነው፡፡ ይህ እንጉርጉሮ በተለምዶ “ማለሁ” እየተባለ የሚጠራው ነው (አል-ካብሊ እንጉርጉሮውን “ማለሁ” በማለት ነው የሚጀምረው፤ ዐረብኛ እንዲህ ሲባል “ለምን ሲል ነው?” የሚል ዘይቤአዊ ፍቺ አለው)፡፡ ታዲያ አል-ካብሊ ብዙ ጊዜ ዘፈኑን ከእንጉርጉሮው በመለየት ነው የሚጫወተው፡፡ አንዳንዴ ግን ሁለቱንም በአንድ ላይ ይዘፍናቸዋል፡፡ ሁለቱ ግጥሞች ሲዘፈኑ የተለያየ የድምጽ ውጣ-ውረድን ስለሚጠይቁ ማንም ዘፋኝ ነኝ ባይ በአንድ ላይ ሊዘፍናቸው ይቸገራል፡፡ እኔ ባለኝ ልምድ ግን አንድ ሰው ሁለቱንም በአንድነት ዘፍኖአቸው ተሳክቶለት አይቼአለሁ፡፡
አዎን! ዓሊ ቢራ ነው፡፡ ዓሊ በ1998 የእንቁጣጣሽ በዓልን በማስመልከት በሸራተን አዲስ በተዘጋጀው የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ እንጉርጉሮውንና ሸዛ ዛህርን አንድ ላይ ዘፍኖአቸዋል፡፡ የዓሊ ቢራ አዘፋፈን ውብ መሆኑን ለማየት በዩ-ቲዩብ ላይ የተጫነውን ቪዲዮ ይመልከቱ፡፡
(ቪዲዮውን ለማለት የሚከተለውን ሊንክ ክፈቱ)፡፡
በነገራችን ላይ ዓሊ ቢራ “ሸዛ ዛህር”ን ብቻ ሳይሆን ሌሎች የሱዳን ዘፈኖችንም ሲጫወት በጣም ይሳካለታል፡፡ የዚህ ስኬት አንደኛው ምክንያቱ ደግሞ ዓሊ ግጥሞቹ የተጻፉበትን “ዐረቢያ አል-ፍስሓ”ን በትክክል መናገር የሚችል መሆኑ ነው፡፡ (ዐረቢያ አል-ፉስሓ ሃያ ስምንቱን የዐረብኛ ድምጾች በትክክል ማውጣትን ይጠይቃል)፡፡
*****
አፈንዲ ሙተቂ
ህዳር 18/2007


ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
እነሆ በድጋሚ ወደ ተረት ዓለም ልወስዳችሁ ነው፡፡ ድሮ የሰማሁት አንድ ተረት ከሰው ልጅ ደካማ ባህሪያት መካከል የሚቆጠረውን “ጥጋብ”ን በተዋበ መንገድ እንዴት እንደሚሄሰው እዩት፡፡
—–
በአንዲት መንደር የሚኖር አንድ ደሃ ሰው የሚበላውን እያጣ ይቸገር ነበር፡፡ ሰውዬው ብዙ ዘመን በችግር ካሳለፈ በኋላ “በተወለድኩበት ምድር በረሃብ ከምሞት ወደ ሌላ ሀገር ልሂድና ሲሳዬን ልፈልግ” በማለት ተሰደደ፡፡ ብዙ ከሄደ በኋላ ድካም ሲጀምረው ከአንድ ዛፍ ስር አረፍ አለ፡፡ ልክ እንደተቀመጠም ከዛፉ ላይ የነበረችው አንዲት በቀቀን “ጥጋብ አይቻልም” እያለች መዘመር ጀመረች፡፡ ሰውዬውም ወደላይ እያንጋጠጠ “እንዲህ ስትይ አታፍሪም እንዴ?! ረሃብ ነው የማይቻለው እንጂ ጥጋብማ በደንብ ነው የሚቻለው” በማለት አጸፋውን መለሰላት፡፡
  ሰውዬው የሚበቃውን ያህል ካረፈ በኋላ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ ብዙ ከተጓዘ በኋላም ወደ አንዲት ትንሽ ከተማ ገባ፡፡ እዚያም ልመናውን ጀመረ፡፡ ብዙ ቤቶችን አዳረሰ፡፡ የከተማዋ ሰዎችም ያላቸውን ሰጡት፡፡ ሰውዬው ምሽቱን ከአንድ በረንዳ ስር አሳለፈ፡፡ በማግስቱም ልመናውን በመቀጠል ከአንድ ሰፊ ግቢ ደረሰ፡፡ እዚያም “ስለ አላህ! ያላችሁን ስጡኝ! ተዘከሩኝ” በማለት ልመናውን ተያያዘው፡፡ የቤቱ ባለቤት የግቢውን በር ከፈተችና ለማኙን አየችው፡፡ ሰውዬው ከመጎሳቆሉ በስተቀር መልከ መልካም ነው፡፡ አንድም የአካል ጉዳት የለበትም፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሰው መለመኑ ስላስገረማት “አንተ ሰው! እንደዚህ ጤነኛ ሆነህ ነው እንዴ የምትለምነው?” አለችው፡፡ “ምን ላድርግ እመቤቴ ተቸግሬ ነው እኮ!” በማለት መለሰላት፡፡
“ለምን ሰርተህ አትበላም?”
“ስራ የለኝም፤ ትናንት ነው ከሌላ ሀገር የመጣሁት”
“እና ልትለምን ነው የመጣኸው?”
“አዎና እመቤቴ! ስራ የለኝም እኮ”
“ስራ ቢሰጥህ ትሰራለህ?”
“አዎን እሰራለሁ”
ሴትዮዋ የሀብታም ሰው ሚስት ነበረች፡፡ ባሏ በድንገት ሲሞትባት ከባሏ በወረሰችው ገንዘብ እየነገደችና እያስነገደች ትኖር ነበር፡፡ በመሆኑም ለማኙን ሰውዬ ከሌሎች ተቀጣሪዎቿ ጋር እንዲሰራ ፈቀደችና ወደ ግቢዋ አስገባችው፡፡ ከዚያም የለበሰውን ቡትቶ እንዲያወልቅ በመንገር አዲስ ልብስ እንዲሰጠው አደረገች፡፡ የሚኖርበትም ቤት ተሰጠው፡፡ ቀለብም ተቆረጠለት፡፡ ሰውዬወም በሴትዮዋ ለጋስነት እየተገረመና ምስጋና እያቀረበ የተመደበለትን የሱቅ አሻሻጭነት ስራ መስራት ጀመረ፡፡
 ሰውዬው ከስራው ጋር በጥቂት ጊዜ ውስጥ ተለማመደ፡፡ በስራው ውስጥ ከሁሉም ሰራተኞች በላጭ ሆኖ ተገኘ፡፡ በታማኝነቱም የተመሰገነ ሆነ፡፡ ሴትዮዋ በሰውዬው ባተሌነትና በታማኝነቱ ልቧ ተነካ፡፡ እያደርም በፍቅሩ ተነደፈች፡፡ ብዙ አውጥታ ካወረደች በኋላም ልታገባው ወሰነች፡፡ እናም ለሰውዬው ይህንኑ ነገረችው፡፡
   ይሁንና ሰውዬው በሴትዮዋ አባባል አኮረፈ፡፡ “እኔ ከትቢያ ላይ የተነሳሁ አንድ ድሃ ሰው ነበርኩ፤ እንዴት ካንቺ ጋር በጋብቻ መተሳሰር እችላለሁ?” አላት፡፡ ሴትዮዋ ምክንያቱን ነገረችው፡፡ ከብዙ ክርክር በኋላ ሰውዬው ሊያገባት ወሰነ፡፡ በመሆኑም ድል ያለ ድግስ ተደግሶ ያ የጥንት ለማኝ የቤቱ አባወራ ለመሆን በቃ፡፡
ሰውዬው አባወራ ከሆነ በኋላም ኃላፊነቱን በትጋት መወጣቱን ቀጠለ፡፡ ሴትዮዋም ይበልጥ እያፈቀረችው ሄደች፡፡ “ይሄ ሰውዬ ለምንጊዜውም የሚከዳኝ አይመስለኝም፤ ስለዚህ የስራውን ኃላፊነት በሙሉ ለርሱ ልስጠው፤ ትንሽ ቆይቼ ደግሞ ድርጅቱን በርሱ ስም አዛውራለሁ” በማለት ወሰነች፡፡ ከዚያም ሰውዬውን ጠራችና እንዲህ አለችው፡፡
“እስከዛሬ ድረስ እንደ ሰራተኛም እንደ ባልም ሆነህ ጥሩ ጊዜ ከኔ ጋር አሳልፈሃል፤ ባሳየኸኝ ታማኝትና በሰጠኸኝ ፍቅር ሙሉ ደስተኛ ነኝ፡፡ ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ የድርጅቱ ሃላፊም ሆነ ተቆጣጣሪ አንተ ነህ፤ ካንተ በላይ ማንም የለም፤ እኔ ራሴ በአንተ ስር ነኝ” አለችው፡፡ይህንን ካለችው በኋላ የድርጅቱን አስፈላጊ ሰነዶች አስረከበችው፡፡ በቤቷ የሚገኙ የካዝና ቁልፎችንም ስታስረክበው እንዲህ አለችው፡፡
  “እኝሁልህ የካዝናዎቻችን መቆለፊያዎች! ከዛሬ ጀምሮ ባንተ ኃላፊነት ስር ሆነዋል፤ ወርቁም ሆነ አልማዙ በብዛት አለልህ፤ ነገር ግን የአንዱን ካዝና ቁልፍ አልሰጥህም፤ በዚያ ውስጥ ምን እንዳለ እንድትጠይቀኝም አልፈቅድልህም፤ እርሱን የጠየቅከኝ እለት መቆራረጣችንን እወቅ”፡፡ ሰውዬውም ስለጉዳዩ ምንም ነገር ላይጠይቃት ቃሉን ሰጣት፡፡ በመሃላ ጭምር አረጋገጠላት፡፡
    ባልና ሚስቱ እንዲህ ከተግባቡ በኋላ ኑሮአቸው ደራ፡፡ ትዳራቸው ይበልጥ ተሟሟቀ፡፡ ድርጅታቸው በትርፍ ላይ ትርፍ መዛቁን ቀጠለ፡፡ ሰውዬውም ምንም ተቆጣጣሪ ሳይኖረው ገንዘቡን እንዳሻው ያወጣ ጀመር፡፡ እያደር ግን የሰውዬው ልብ መቀየር ጀመረች፡፡ በአንድ ካዝና እና በውስጠ ሚስጥሩ ላይ ጥያቄ እንዳያቀርብ የተጣለበትን እግድ ሲያስታውስ ገና የሀብት ጣሪያ ላይ ያልደረሰ ሆኖ ተሰማው፡፡ ያንን ካዝና ከፍቶ አለማየቱም ያንገበግበው ጀመር፡፡ ሴትዮዋ አንዱን ካዝና ነጥላ በማስቀመጧም “እወድሃለሁ የምትለው ከልቧ አይደለም” በማለት ወቀሳት፡፡ በመሆኑም ካዝናውን ከፍቶ ለማየት ተመኘ፡፡ ወደሴትዮዋ ሄዶም ጥያቄውን አቀረበ፡፡
   
  ሴትዮዋ በጥያቄው ተደናገጠች፡፡ ተገረመችም፡፡ ቃሌን ያከብራል ብላ የገመተችው ሰው ቃል አባይ ሆኖ በመገኘቱ ተናደደችበት፡፡ ነገር ግን ከሰውዬው ፍቅር ስለያዛት የመጨረሻ እድል ልትሰጠውና ከመንገዱ ልትመልሰው ወሰነች፡፡ እንዲህም አለችው፡፡
   “አረ አንተ ሰው የፈጠረህን ፍራ! ስለዚህ ካዝና ጉዳይ አንድም ጥያቄ ላትጠይቀኝ ቃል ኪዳን ሰጥተህኛል እኮ፤ እባክህ ይህንን ጥያቄህን ተውና በሰላም አብረን እንኑር”
“አንቺ ራስሽ እወድሃለሁ የምትይው ከልብሽ አይደለም፤ ያንን ካዝና ከፍተሸ ከውስጡ ያለውን ነገር ካላሳየሽኝ አትወጂኝም ማለት ነው”
“አረ አንተ ሰው መሀላ አታፍርስ! እረፍልኝ ብዬሃለሁ”
“የካዝናውን ቁልፍ እንድትሰጭኝ እፈልጋለሁ”
ሴትዮዋ ተናደደች፤ ነገር ግን ሰውዬውን ስለምትወደው በሽማግሌ ልታመስክረው ሞከረች፡፡ ሽማግሌዎችም “መሃላህን አትብላ! የፈጣሪ ቁጣ ይወርድብሃል፤ እንደ ድሮው በሰላም ብትኖሩ ይሻላል” አሉት፡፡ ሰውዬው ግን “ካዝናው ካልተከፈተ ሞቼ እገኛለሁ” በማለት ሙግቱን አፋፍሞ ቀጠለ፡፡ ሴትዮዋም በነገሩ ተስፋ ቆረጠች፡፡ ሰውዬው ወደ ኋላ የማይመለስ መሆኑን ካረጋገጠች በኋላ የከተማዋ ሽማግሌዎችና ታዋቂ ሰዎች እንዲሰበሰቡ አደረገች፡፡ ከዚያም ካዝናውን ከፈተችውና ከውስጡ ያለውን እቃ አወጣች፡፡ በሀይለ ቃልና በቁጭት በሰውዬው ፊት ላይ ወረወረችው፡፡
———-
ከካዝናው ውስጥ የተገኘው እቃ ሰውዬው ከሀገሩ የመጣበት ቡትቶ ልብስ እንጂ እንቁ ወይንም ሌላ የከበረ ጌጣጌጥ አልነበረም፡፡ ሴትዮዋ ለክፉ ቀን መጠባበቂያ እንዲሆናት ነው ከካዝና ውስጥ የቆለፈችበት፡፡ እውነተኛው ቀን ሲደርስ ልብሱን እዚያ ማስቀመጧ ትክክል እንደሆነ ተረዳች፡፡ ልብሱን በሰውዬው ፊት ላይ ከወረወረችለት በኋላም እንዲህ አለችው፡፡
“አንተ ውለታ ቢስ! ቶሎ ብለህ የኔን ልብስ አውልቅ! አንተ ያመጣኸውን ልብስ ልበስና ከዚህ ቤት ጥርግ ብለህ ጥፋልኝ”
ሰውዬው በድንጋጤ ክው ብሎ ቀረ፡፡ ከትቢያ ተነስቶ በተከበረበት ከተማ መዋረዱ ከፍተኛ እፍረት ውስጥ ጣለው፡፡ በመሆኑም ከከተማዋ በደረቅ ሌሊት ጠፋ፡፡ ወደ ሀገሩ ሊመለስም ጉዞውን ተያያዘው፡፡ ረጅም ርቀት ከተጓዘ በኋላ በቀቀኗን ካገኘበት ቦታ አረፈ፡፡
  ታዲያ በቀቀኗ “ጥጋብ አይቻልም” እያለች የድሮውን መዝሙር መዘመሯን እንደቀጠለች ነው፡፡ ሰውዬውም “እውነትሽን ነው! ጥጋብን ከእግር እስከ ራሱ አይቼው የማልችለው ዐይነት ሲሆንብኝ ወደ ድሮው የድህነት ህይወቴ እየተመለስኩ ነው” አላትና የመዝሙሩን ሐቀኛነት አረጋገጠላት፡፡
———–
አይጣል ነው መቼስ! በርግጥም ጥጋብ አይቻልም፡፡ በእውነታው ዓለም የተከሰቱ በርካታ ታሪኮችን ከዚህ ጋር ማነጻጻር ይቻላል፡፡ ሀብትን ስናገኝ  አዕምሮአችን ከርሱ ጋር ካላደገ የሰራነው ሁሉ ወደ ዜሮ ሊመልስብን ይችላል፡፡ ለሁሉም ግን ፈጣሪያችን ከእንዲህ ዓይነቱ ክፉ እጣ ይሰውረን!
አሚን!
——
መጋቢት 19/ 2006
አፈንዲ ሙተቂ
(ተረቱን ያጫወቱኝ የገለምሶ ትልቁ መስጊድ ኢማም የሆኑት ሼኽ ሙኽታር አሊይ ናቸው፤ ዘመኑም እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር 1988 ነበር፤ ሼኽ ሙኽታር በአሁኑ ጊዜ የ85 ዓመት አዛውንት ናቸው፤ አላህ ጤናውንና ብርታቱን ይጨምርላቸው)፡፡


 ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
—–
“ሀረር ጌይ” በተሰኘው መጽሐፌ ውስጥ “ሀረር የባግዳድ እህት ናት” የሚል የረጅም ጊዜ ልማድ እንዳለ አጫውአችኋለሁ፡፡ ይህም አመለካከት የመጣው ሁለቱ ከተሞች የሚመሳሰሉ በመሆናቸው ነው፡፡ ከተሞቹን ከሚያመሳስሏቸው የህይወት ዘርፎች መካከል አንዱ እምቅ የስነ-ቃል ሀብታቸው ነው፡፡ ከነዚህ የስነ-ቃል ሀብቶች ቀዳሚ ሆኖ የሚጠቀሰው ተረት ነው፡፡ የባግዳድ ተረቶችን በ“አንድ ሺህ አንድ ሌሊት” በኩል አንብበናቸዋል፡፡ የሀረር ተረቶች ግን በመጽሐፍ ያልተሰበሰቡ በመሆናቸው ከብዙኃኑ አንባቢ ዘንድ ሊደርሱ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ እነርሱንም በመጽሐፍ የሚሰበስብ የብዕር ጀግና ያስፈልገናል፡፡
በዚህ ጽሑፍ ሁለት የሀረር ተረቶችን አጋራችኋለሁ፡፡ ሁለቱንም ተረቶች በልጅነቴ የማውቃቸው ቢሆንም በሀረር ከተማ ቆይታዬ በአዲስ መልክ ሰምቼአቸዋለሁ፡፡  
የሓኪም ጋራ መሰንጠቅ
በጥንት ዘመን ሀረር በድርቅ ተመታች፡፡ በድርቁ ሳቢያም ምንጮቿና ወንዞቿ ደረቁ፡፡ አንድ “ኤላ” (የውሃ ጉድጓድ) ግን በተአምራዊ መንገድ ከመጥፋት ተረፈ፡፡ ይሁንና መገኛው ያልታወቀ ትልቅ ዘንዶ ከጉድጓዱ አፋፍ ተቀምጦ “ኤላው የኔ ነው” በማለቱ ከኤላው ውሃ መቅዳት አስቸጋሪ ሆነ፡፡ የሀረር ህዝብ ከኤላው ውሃ መቅዳት ከፈለገ በየዓመቱ አንዲት ቆንጆ ወጣት መገበር እንዳለበት ዘንዶው በአዋጅ አስታወቀ፡፡ የመጠጥ ውሃ ማግኘት የቸገረው የሀረር ህዝብም አማራጭ ሲያጣ ለዘንዶው በመገበር ከኤላው ውሃ ለመቅዳት ተገደደ፡፡
ለዘንዶው የምትሰጠው ልጅ በእጣ ነው የምትወሰነው፡፡ እጣው የሚወጣበት ሁኔታ ግን ፍትሐዊ አልነበረም፡፡ የሀብታምና የባለስልጣናት ልጆች በስውር ዘዴ ከእጣው ውጪ እንዲሆኑ ይደረግና የድሃ ልጆች ብቻ እየተመረጡ ለዘንዶው ይሰጣሉ፡፡ ድሆቹ ይህንን በደል ቢያውቁትም ከሀብታሞቹ ጋር መፎካከር ስለማይችሉ ልጆቻቸውን ለዘንዶው እየገበሩ እምባቸውን መርጨት ግዴታ ሆነባቸው፡፡
ታዲያ በአንድ ዓመት ልጅ የመገበሩ እጣ የደረሰው ለአንዲት “ተቂይ” (አላህን የምትፈራ) ሴት ነው፡፡ ያቺ ሴት አንዲት ልጅ ብቻ ነበራት፡፡ ልጅቷንም ያገኘችው በስተእርጅና ሲሆን ባለቤቷ ከልጅቷ መወለድ በኋላ ሞቶባታል፡፡ በመሆኑም ሴትዮዋ አንድዬ ልጇን እንደ እናትና እንደ አባት ሆና ነው ያሳደገቻት፡፡  እንግዲህ እነዚያ እጣ አውጪዎች ሴትዮዋ በስተእርጅና ያገኛትንና በድህነት ያሳደጋችትን ያቺኑ ልጅ ለዘንዶው እንድትገብር ነው የፈረዱት፡፡
   ይሁንና ሴትዮዋ ልጇን ለዘንዶው አላስረክብም አለች፡፡ የሰፈሯ ሰዎች “እምቢ ካልሽ እኮ ዘንዶው አንቺንም ጨምሮ ይበላሻል” እያሉ ቢያስፈራሯትም ሴትዮዋ ወይ ፍንክች በማለት በቃሏ ጸናች፡፡ ሰዎቹም “በቃ! ውርድ ከራሳችን!! ዘንዶው ቢበላሽ ተጠያቂ አይደለንም” በማለት ብቻዋን ተዋት፡፡ ወደ ዘንዶው ሄደውም ስለሴትዮዋ እምቢተኝነት ነገሩት፡፡ ከዚያም በየቤታቸው ሆነው ተከታዩን ነገር መጠባበቅ ጀመሩ፡፡ ሴትዮዋም ልጇን ከምታስረክብበት ዕለት በፊት ባለው ምሽት የዘንዶውን ጭካኔና የእጣ አውጪዎቹን አሻጥር እያነሳች ፈጣሪዋን ስትለምን አደረች፡፡ በማግስቱም ከቤቷ ቁጭ ብላ ዘንዶው የሚያመጣውን መቅሰፍት መጠባበቅ ጀመረች፡፡
 ሴትዮዋ ልጇን የምታስረክበው ከጧቱ በሶስት ሰዓት ገደማ የነበረ ቢሆንም ዘንዶው በሰዓቱ ግብሩን አላገኘም፡፡ በዚህም የተናደደው ዘንዶ ሴትዮዋን ከነልጅቷ ሊውጣት እጅግ በሚያስፈራ ግርማ ወደ ቤቷ መጓዝ ጀመረ፡፡ የሰፈሩ ሰዎችም “ሊበላት ነው፤ ሴትዮዋ አለቀላት!” እያሉ በአድናቆትና በተመስጦ ትርዒቱን ይመለከቱ ገቡ፡፡
ዘንዶው አቧራውን እያቦነነ ከሴትዮዋ ቤት አጠገብ ደረሰ፡፡ ሴትዮዋንም ሊውጣት መንደርደር ጀመረ፡፡ ፍላጎቱን ከመፈጸሙ በፊት ግን ፈጣሪ ውጥኑን አከሸፈበት!! እጅግ ግዙፍ የሆነ ንስር (አሞራ) ከሀረር በስተሰሜን አቅጣጫ በመምጣት ዘንዶውን ከመሬት ላይ “ላጥ” አድርጎ አነሳው፡፡ ንስሩ ዘንዶውን ወደ ሰማይ በማውጣት ላይ ሳለም የዘንዶው ጭራ ሀረርን በደቡብ በኩል የከበበውን የሀኪም ጋራን በሁለት ቦታ ከፈለው፡፡
 
  ያ ከይሲ ዘንዶ ፈጣሪዋን የምትፈራው ሴትዮ ባደረገችው ጸሎት ተወገደ፡፡ በሀረር ከተማ ላይ የተጣለው ልጅን የመገበር ግዴታም ለዘልዓለሙ ተነሳ!! ይሁንና ያኔ በዘንዶው ጭራ የተከፈሉት ሁለቱ የሐኪም ጋራ ኮረብቶች በአንድ ላይ ሳይመለሱ እስከዚህ ዘመን ድረስ ዘለቁ፡፡
አሚር ሆይ! አንተ “ኸይሩ”ን ብቻ አስብ፤ “ለሸሩ” ባለቤት አለውና!!
——
በጥንት ዘመን አንድ ቅን ሰውዬ በሀረር ከተማ ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ የመጀመሪያው ልጁ ርህሩህና የዋህ የነበረ ሲሆን ሁለተኛው ልጁ ግን ተንኮል እየፈጠረ ሰዎችን ማሞኘትና መሳቅ ይወድ ነበረ፡፡ አባትዬው ትንሹን ልጅ ቢመክረው አልሰማ እያለ አስቸገረው፡፡ ስለዚህ በትንሹ ልጅ ተስፋ የቆረጠው አባት ዘወትር ትልቁን ልጅ እየጠራው “ልጄ ሆይ! አንተ ደጉን ብቻ አስብ፡፡ ለተንኮል ባለቤት አለውና” የሚል ምክር ይሰጠው ነበር፡፡ አባት በዚህም ሳያበቃ ለትልቁ ልጅ “ዓሊ ኸይሮ” (ቅን አሳቢው ዓሊ) የሚል ቅጽል አወጣለት፡፡ ትንሽየውን ግን “ዓሊ ሸርሮ” (ተንኮለኛው ዓሊ) በማለት ሰየመው፡፡
 
   ከጊዜ በኋላ አባት የአዱኛውን ዓለም ተሰናበተ፡፡ በዚህም የተነሳ ልጆቹ ተቸገሩ፡፡ ኑሮ በጣም ከበዳቸው፡፡ በመሆኑም ወደ ሀረሩ አሚር ሄደው በችግር መቆራመዳቸውን ነገሩት፡፡ አሚሩ በአጋጣሚ የቤተ መንግሥት ከብቶችን የሚጠብቅ ሰው ይፈልግ ነበርና ወንድማማቾቹ ለእረኝነት እንዲቀጠሩ ጠየቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹ ለስራው የሚሰጣቸውን ምንዳ ሲጠይቁት ከሚበሉት ምግብና ከሚለብሱት ልብስ በተጨማሪ በዓመቱ መጨረሻ ላይ አንዲት ጊደር እንደሚያገኙ አሳወቃቸው፡፡ ወንድማማቾቹም ከአሚሩ የቀረበላቸውን ጥያቄ በደስታ ተቀበሉትና ስራቸውን ጀመሩ፡፡
ወንድማማቾቹ በመቶዎች የሚቆጠሩትን የአሚሩን ከብቶች “አው-ሓኪም”፣ “አቦከር” እና “ሸድዳ ዋ መድዳ” ወደሚባሉት ተራሮች እያሰማሩ በትጋት ማገዱን ተያያዙት፡፡ ስራቸውን በደህና ሁኔታ እያከናወኑ ዓመቱን አገባደዱት፡፡ የዓመቱ መጨረሻ እየተቃረበ ሲመጣ ግን የ“አሊ ሸርሮ” ልብ በግለኝነት መመታት ጀመረች፡፡ ለምንዳ የምትሰጣቸውን ጊደር ጉዳይ ሲያስብ አዕምሮው በስስት ተወጠረ፡፡ በመሆኑም “ወንድሜን ገድዬው ጊደሪቱን የግሌ ማድረግ አለብኝ” በማለት ወሰነ፡፡ እቅዱንም በአው ሓኪም ተራራ ላይ ለመፈጸም ቆረጠ፡፡
ወንድማማቾቹ ከብቶቹን ወደ “ሓኪም” ተራራ በወሰዱበት በአንደኛው ቀን “አሊ ሸርሮ” ለወንድሙ “አንተ ከዚህ ሆነህ ከብቶቹን ጠብቅ፤ እኔ ተራራው ላይ ወጥቼ ለምለም ሳር እንዳለ ልይና ልመስ” አለው፡፡ “አሊ ኸይሮ”ም በቀረበለት ሃሳብ ተስማምቶ ከብቶቹን ለብቻው መጠበቅ ጀመረ፡፡ “አሊ ሸርሮ” ከተራራው ላይ እንደ ወጣ ትልቅ ድንጋይ አንቀሳቅሶ ወንድሙ ወዳለበት አቅጣጫ ቁልቁል ለቀቀው፡፡ ድንጋዩ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ ወረደ፡፡ ከ“አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ ግን ወደ ወርቅነት ተቀየረ፡፡ “አሊ ኸይሮ” በዚህ ተአምር ተገረመ፡፡ “ወደ ወርቅነት የተቀየረው ድንጋይ እኔና ወንድሜ ሀብታም እንድንሆን ዘንድ ከአላህ የተሰጠን ነው” በማለት በደስታ ፈጣሪውን አመሰገነ፡፡ የተፈጠረውንም ተአምር ለወንድሙ ለመንገር በጉጉት ይጠባበቅ ጀመር፡፡
 
 “አሊ ሸርሮ” በበኩሉ “አሊ ኸይሮ በድንጋይ በመገደሉ “ጊደሪቱ የኔ ብቸኛ ሀብት ትሆናለች” እያለ በደስታ ከተራራው ወረደ፡፡ ወንድሙ ወደነበረበት ቦታ ሲደርስ ግን ያልጠበቀውን ነገር አየ፡፡ “ይህ ወርቅ ከየት ነው የመጣው?” በማለትም ወንድሙን ጠየቀው፡፡ አሊ ኸይሮም “አንድ ትልቅ ድንጋይ ከተራራው ላይ እየተንከባለለ መጥቶ እኔ ጋ ሲደርስ ይህንን ወርቅ ሆነ” በማለት መለሰለት፡፡ “አሊ ሸርሮም “ድንጋዩ የተንከባለለው ከስሩ የነበረውን ለምለም ሳር ለማየት ብዬ ስላንቀሳቀስኩት ነው፤ እዚህ ደርሶ ወደ ወርቅ ከተቀየረ እኔም የራሴ ወርቅ ሊኖረኝ ይገባል፡፡ ስለዚህ አንተም በተራህ ወደ ተራራው ውጣና ሌላ ድንጋይ አንከባልልኝ” አለው፡፡
“አሊ ኸይሮ”ም ከወንድሙ የሰማውን ሳይጠራጠር ወደ ተራራው ወጥቶ ትልቅ ድንጋይ አነሳና “አሊ ሸርሮ” ወደነበረበት አቅጣጫ አንከባለለው፡፡ ይሁንና ድንጋዩ ወደ ወርቅነት ሳይቀየር “አሊ ሸርሮ”ን ጭፍልቅ አድርጎ ገደለው፡፡ “አሊ ኸይሮ” ከተራራው ወርዶ ወንድሙ ወደነበረበት ስፍራ ሲሄድ ወንድሙ ሞቶ አገኘው፡፡ በዚህም በጣም ደነገጠ፡፡ ወደ ሀረሩ አሚር ሄዶም የተከሰተውን ሁሉ አንድ በአንድ ነገረው፡፡ ሆኖም አሚሩ ሊያምነው አልቻለም፡፡ “ወንድምህን ራስህ ነህ የገደልከው” በማለትም ከሰሰው፡፡ በመሆኑም “ነፍስ ያጠፋ ሰው ይገደል” በሚለው የሀረር ከተማ ጥንታዊ ህግ መሰረት በድንጋይ ተጨፍልቆ እንዲሞት ተፈረደበት፡፡
 
“አሊ ኸይሮ”ም ፍርዱ ሊፈጸምበት ወደ “ሐኪም” ተራራ ግርጌ ተወሰደ፡፡ ከተራራው ላይ ትልቅ ድንጋይ ተንዶ ቁልቁል ተወረወረበት፡፡ ይሁንና ድንጋዩ “አሊ ኸይሮ” አጠገብ ሲደርስ እንደገና ወርቅ ሆኖ ቁጭ አለ፡፡ የቅጣቱን አፈጻጻም ለማየት በስፍራው ተሰብስቦ የነበረው የሀረር ህዝብም በተፈጠረው ነገር በጣም ተገረመ፡፡ “ይህ ተአምር ልጁ ወንድሙን እንዳልገደለ በሐቅ ይመሰክራል” በማለትም ደመደመ፡፡ የሀረሩ አሚር በበኩሉ “የዓሊ ኸይሮ”ን ተአምር ሲያይ “በህይወቴ ስፈልገው የነበረውን ሐቀኛ ሰው ዛሬ አገኘሁት” የሚል ቃል ተናገረ፡፡ “አሊ ኸይሮ”ንም የዙፋኑ ወራሽ በማድረግ ሾመው፡፡
—–
ወደ ሀረር ከተማ ከመጣችሁ “Amiroo! Kheyruma yaadi, Sharriin abbuma eeydii” የሚል አባባል ትሰማላችሁ፡፡ “አሚር ሆይ! አንተ ኸይሩን ብቻ አስብ፤ ለሸርሩ ባለቤት አለውና” እንደማለት ነው፡፡ ከአባባሉ ጀርባ ብዙ ታሪኮች ይነገራሉ፡፡ ከነዚያ ታሪኮች መካከል አንዱ ከላይ የቀረበው ተረት ነው፡፡
 በተረቱ እንደተገለጸው ተንኮለኛ ሰው በለስ የቀናው መስሎት ብዙ የሸር ትብታቦችን ሊተበትብ ይችላል፡፡ ይሁንና እንደዚህ ዓይነቱ ሰው አጓጉል ሆኖ ነው የሚቀረው፡፡ የማታ ማታ ራሱ በሸረበው የተንኮል ድር መታሰሩ የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህ በህይወት እያለ ደግ ደጉን ብቻ አስብ!! ለተንኮሉ ባለቤት አለውና!!
በድጋሚ Amiroo kheyruma yaadi, Sharriin abuma eeydi ብለናል፡፡
—-
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 20/2007
—–
The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.  You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click the following link to go to his page.
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 8/2007
ሀረር-ምስራቅ ኢትዮጵያ

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

                                                       
—-

 እነሆ ነፍስ የሆነውን አርቲስት ልናነሳው ወደድን!! ተወዳጅ፣ ጥበበኛ፣ ባለ ተሰጥኦ ከያኒ!! እውነተኛ የሙዚቃ ቀማሪ! ሱዳን ያፈራችው የምንጊዜም ጌጥ!! ከካይሮ እስከ ዑጋንዳ፣ ከጅቡቲ እስከ ማሊ ምንጊዜም እንደተወደደ ያለ የጥበብ ዋርካ!! ሙሐመድ ወርዲ!!

  “ወርዲ” ማለት ለሱዳኖች ንጉሥ እንደማለት ነው፡፡ እኛም ከአንጋፋ አርቲስቶቻችን ነጥለን አናየውም፡፡ በድሮ ጊዜ ወርዲን በፍቅር ሰምተነዋል፡፡ ዛሬም ወርዲን በመደጋገም እየሰማነው ነው፡፡

*****

ወርዲ ከልቡ ዘፋኝ ነው፡፡ ዘፈኖቹ ከኛ ጋር ከመዛመዳቸው የተነሳ እኛን እኛን ይሸታሉ፡፡ በርካታ ዜማዎቹ እኛ የምንጊዜም ምርጦች አድርገን ለምንወዳቸው ታዋቂ ዘፈኖቻችን መነሻ ለመሆንም በቅተዋል፡፡ ለምሳሌ አንጋፋው ድምጻዊ ጥላሁን ገሠሠ ያዜመውን “አንቺ ከቶ ግድየለሽም”ን ውሰዱት፡፡

አንቺ ከቶ ግድ የለሽም

ስለፍቅር አይገባሽም

ሁሉን ነገር እረስተሽው

ችላ ብለሽ ስለተውሽው

ቻልኩት ፍቅር ለብቻዬ፡፡

አዎን! ዛሬም ድረስ የዚህ ዜማ ተወዳጅነት አልቀነሰም፡፡ ለዚህ ዜማ መሰረቱ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ነው፡፡ ሙሐመድ ወርዲ ዘፈኑን ሲያዜመው እንዲህ ነበር ያለው፡፡

“አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ

ጠል ዐዛበክ ዋ ሱሃዲ

ዋ ሽጃያ አነ ዐዛቢ”

ታዲያ ሙሐመድ ወርዲ የተጫወተውን ዜማ ጋሽ ጥላሁን ወደ አማርኛ የመለሰው እንዲሁ በጋጠወጥነት አይምሰላችሁ፡፡ በነገሩ ውስጥ  የወርዲ ሙሉ ቡራኬ አለበት፡፡ በቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ዘመን የካርቱም መንገድ ለኛ አርቲስቶች የውሃ መንገድ ነበረ፡፡ ለሱዳኖችም ከዋዲ ሃልፋ ይልቅ ሸገር ነበር የምትቀርባቸው፡፡ እናም በዚህ ምልልስ መሀል የኛዎቹ አንጋፋዎች (ጥላሁን ገሠሠ፣ ምኒልክ ወስናቸው፣ አለማየሁ እሸቴ፣ ዓሊ ሸቦ፣ ዓሊ ቢራ ወዘተ..) እና የሱዳኖቹ አንጋፋ አርቲስቶች (አሕመድ አል-ሙስጠፋ፣ ሰይድ ኸሊፋ፣ ሙሐመድ ወርዲ፣ አብዱልከሪም አል-ካብሊ፣ አብዱል ዓዚዝ አል-ሙባረክ ወዘተ…) የአንድ ቤተሰብ ልጆች ሆነው ነበር፡፡ ሱዳኖቹ ያዜሙትን የኛዎቹ ወደ አማርኛ፣ ኦሮምኛና ሶማሊኛ እየመለሱ ይጫወቱታል፡፡ የኛንም ዘፈኖች ሱዳኖች በቋንቋቸው እየተረጎሙ ይዘፍኑታል፡፡ አንዳንዴ ዕድል ሲገጥማቸው ሁለቱም ዘፋኞች አንዱን ዜማ በአንድ መድረክ ላይ በየቋንቋቸው ይጫወቱታል፡፡ በዚህ ስሌት መሰረት ነው እንግዲህ የሙሐመድ ወርዲ “አነ ዐርፈክ ያ ፉአዲ” ወደ አማርኛ የተመለሰው፡፡

አዎን!! እነ ጋሽ ጥላሁን እንደ አሁኖቹ ዘፋኞች (አንዳንዶቹን ማለቴ ነው) የሱዳንና የፈረንጅ ዜማን ወደ አማርኛ እየገለበጡ “የራሴ ድርሰት ነው”  ብለው ሊያሞኙን አይከጅሉም፡፡ ዋናው አርቲስት ባለበት ጭምር እየዘፈኑ ያሳዩትና “እንዴት ነው! አበላሽቼብህ ይሆን?” በማለት ምክርና እገዛ ይጠይቁታል፡፡ ሱዳናዊው አርቲስትም በሰማው ነገር ላይ የራሱን አስተያየት ይሰጣል፡፡ የኛዎቹም ከሱዳናዊያኑ አርቲስቶች የሚሰጣቸውን አስተያየት ተንተርሰው እጅግ የተሻለ ስራ ይሰሩና ህዝቡን እንካችሁ ይሉታል፡፡ ለዚያም ነበር ስራው የሚዋጣላቸውና ዘመን ተሻጋሪ የሚሆንላቸው፡፡

በዚህ ስሌት ወደኛ ቋንቋዎች ከተቀየሩት ተወዳጅ የሱዳን ዜማዎች መካከል የጥላሁን ገሠሠ “እዩዋት ስትናፍቀኝ” (ሰይድ ኸሊፋና ኢብራሂም አውድ በጋራ ከዘፈኑት ዘፈን የተወሰደ)፣ የአሰፋ አባተ “ሸግዬ ሸጊቱ” (ከአሕመድ አል-ሙስጠፋ “ሐቢቢ በኪቱ” የተወሰደ)፣ የምንሊክ ወስናቸው “ስኳር” (ከአብዱልከሪም አል-ካብሊ “ሱከር” የተወሰደ) የዓሊ ቢራ “ኦፊ ረፋ ቡልታ” (ከሙሐመድ ወርዲ “ያ ኑረል-ዐይን” የተወሰደ) ይጠቀሳሉ፡፡

                                                                          *****

    በርካታ የሀገራችን የሙዚቃ ወዳጆች ከመሐመድ ወርዲ ዜማዎች መካከል ለ“ገመር ቦባ” እና ለ“ቲስዐተ ዐሸር ሰና” (ብዙዎች የሚያውቁት  “ሰበርታ” በሚለው ስም ነው) ልዩ ፍቅር አላቸው፡፡ ሆኖም ሱዳኖች በአንደኛ ደረጃ የሚያሰልፏቸው ሌሎች በርካታ የወርዲ ዜማዎች አሉ፡፡ በተለይም “ሱድፋ”፣ “ቃሲ ቀልበክ”፣ “አልሀወል አወል”፣ “አነ ማ በንሳክ”፣  “አንናስ አል-ጊያፋ”፣ “ሐረምተ አድ-ዱንያ”፣ “ያ ኑረል ዐይን”፣ “ሸተል ዘማ”፣ “አል-ሙርሳል” የመሳሰሉት ከምርጥ የወርዲ ዜማዎች መካከል ይሰለፋሉ፡፡ እኔ በግሌ በጣም ከምወዳቸው የሱዳን ዜማዎች መካከልም አንዱ የሙሐመድ ወርዲ “አዚብኒ ወተፈነን” ነው፡፡

ዐዚብኒ ወዚድ ዐዘባ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚይክ

ዜይመን ሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይግሳዚክ፡፡

አዚብኒ ወተፈነን ፊ አልዋን ዐዛቢ

ማ ቲምሳሕ ዲሙዒ ማ ቲርሐም ሸባቢ፡፡
ኸሊኒ ፊሹጁኒ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ

ዜይ መንሳኒ ገልበክ ዩምኪን ገልቢ ይክሳዚይክ፡፡

ወርዲ በዚህ ዘፈን ለወዳጁ “ልብሽ ጨክኖብኝ ፍቅርሽ አቃጥሎ እየጨረሰኝ ነው፤ መጥተሸ እምባዬን የማታብሺልኝ ልበ-ደረቅ ነሽ” የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው የፈለገው፡፡ ወርዲ ይህንን ዜማ የዛሬ 20 ዓመት ገደማ በአዲስ አበባ ስታዲየም እጅግ ባማረ ሁኔታ የተጫወተው ሲሆን የሀገራችን አድናቂዎችም በጋለ ስሜት ተቀብለውታል ( ቪዲዮውን በሚከተለው ሊንክ ላይ ተመልከቱት፡፡  https://www.youtube.com/watch?v=WkegFEEwjjM&feature=related

                                                                          *****

ታዲያ የወርዲ ፍቅረኛ በ“አዚብኒ-ወተፈነን” ውስጥ እንደተገለጸው በጭካኔዋ አልዘለቀችም፡፡ ወርዲ በጉንጮቹ ላይ የሚያፈሰው እምባ አሳዝኖአት ከፍቅር በረከቱ ልታቀምሰው መጥታለታለች፡፡ ወርዲም ፍቅረኛውን ያገኘበትን ቀን “የቀኖች ሁሉ ረጢብ፣ እጅግ በጣም ገዳም፣ የምኞቴን ያሳካሁበት ቀን መጥቶልኛል” በማለት ገልጾታል፡፡

“ሱድፋ” የሚለውን የሙሐመድ ወርዲን ዘፈን እናውቀው የለ?.. በዚያ ዘፈን ውስጥ ወርዲ ለወዳጁ ያለውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን ከናፈቁት ወዳጅ ጋር መገናኘቱ የሚሰጠውን ደስታ በተዋቡ ቃላት ገልጾታል፡፡ እኔ በበኩሌ እጅግ በጣም የምወደው የወርዲ ዘፈን ይኸው ሱድፋ ነው፡፡ እነሆ የሱድፋን ሙሉ ግጥም ተጋበዙልኝ፡

ሱድፋ… ሱድፋ

ሱድፈ ወ አጅመል ሱድፈነ የውም ላቄታ

አስዓድ የውም የውሚል ሐዬታ

ኑረ ዐይነያ አያም ሓቤታ

ይህ አዝማቹ ነው እንግዲህ፡፡ “ሱድፋ” ማለት አስገራሚ ዕድል ማለት ነው (በእንግሊዝኛ fortunate የሚለው ቃል ይቀርበዋል)፡፡ ተከታዮቹ ግጥሞች የሚከተሉት ናቸው፡፡

አን-ነዘራት በሪዓ ገመም ዘውፍጀል ኸጀል

አልበሰማት ተበዊ ዘይ ኑረል ዐመል

ወጅሂክ ቤን መዛህሪክ ዘይ በድሪ-ክ-ከመል

ወሽሻመክ ኺዴድክ ዘይ ጠዕመል ኹበል

ተስኪር ገልቢ

ወተሽዒል ሑቢ

ኢሽሀክ ረብቢ

አነ በህ ዋ

—–

ማ ቃዲር አጉል ሊክ አን ሑብቢል ከቢር

ወስፉ ዓለይያ ቃሲ መዓዪሽ ፊ-ድ-ደሚር

ቀድረል ከውን ተኩልሉሁ አክበር ቤ ከቲር

ማሊክኒ ሙሐዪይርኒ ሹፍከል ቢል ኣሲር

አስአሊ ቀልቢ

ኢኪኒ ዪቅደር

ኢሽራሕ ሑቢ

አነ ሙሕታር

——

ሱድፈ ዑዩኑ ሻፈክ ሌይሊ ባቂ ይነዊር

ያ አይያም ረቢዒ ዑምሪ መዓኪ አዝሐር

ፊሃ አጥ-ጤይር ይገኒ ሚን አል-ሓኒ ዪዝከር

ቀልቢ ፈራሸ ሐውሊ ወኢንቲ ሸባቢከ አኽደር

ያ መበሒብቢ

ባዕቡድ ሑብቢክ

አለሻን ሑብቢክ

ሩሒ ፈዳክ

*****

ለመሆኑ መሐመድ ወርዲ ማን ነው?

  ሙሉ ስሙ ሙሐመድ ዑስማን ሳሊሕ ወርዲ ነው፡፡ እርሱ ግን “ሙሐመድ ወርዲ” ወይንም በአጭሩ በቤተሰቡ ስም “ወርዲ” ተብሎ ነው የሚታወቀው፡፡ የተወለደው እ.ኤ.አ. በ1932 “ዋዲ ሀልፋ” በተሰኘው ሰሜናዊው የሱዳን ክፍለ ሀገር፣ “ሱወርዳ” በተባለች ትንሽዬ የገጠር መንደር ውስጥ ነው፡፡ እናቱ የኑቢያ ተወላጅ ስትሆን አባቱ ዐረብ ነው፡፡

ወርዲ የሙት ልጅ ነው፡፡ ሁለቱንም ወላጆቹን በልጅነቱ ነው ያጣው፡፡ በመሆኑም በዘመዶቹ ጥበቃ ስር ሆኖ ነው ያደገው፡፡ ትምህርቱን በዋዲ ሀልፋ እና በካርቱም ተከታትሏል፡፡ የተወለደበትን ሀገር እስከ 1956 በመምህርነት ሙያ ካገለገለ በኋላ በወቅቱ ይሞካክራቸው የነበሩት ዘፈኖች በኦምዱርማን ሬድዮ ጣቢያ ተቀርጸው በመተላለፋቸው በህዝብ ልብ ውስጥ ገባ፡፡ ያገኘው የሞራል ድጋፍ ማነሳሻ ስለሆነው መምህርነቱን ትቶ የአርቲስትነቱን ጎራ ተቀላቀለ፡፡ ከዚያም ሱዳኖች ከሚያፈቅሯቸው ቁንጮ ዘፋኞቻቸው አንዱ ለመሆን በቃ፡፡

 

    ወርዲ በህይወቱ የተረጋጋ ኑሮ አልኖረም፡፡ በሱዳን የተለዋወጡት መንግሥታት በተቃዋሚነት እየፈረጁት አንገላተውታል፡፡ በመሆኑም ለሀያ ዓመታት ያህል በካይሮና በለንደን ነው የኖረው፡፡ በ2002 ግን ወደ ሀገሩ በክብር ተመልሷል፡፡ ወርዲ በሙዚቃው ዕድገት ላደረገው አስተዋጽኦ ከካርቱም ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸልሟል፡፡ ከልዩ ልዩ የአውሮጳ፣ አፍሪቃና እስያ ሀገራትም ሽልማቶችን ተቀብሏል፡፡

 መሐመድ ወርዲ በመጨረሻዎቹ ዓመታት በደረሰበት የጤና መታወክ ሁለት ኩላሊቶቹ ከጥቅም ውጪ ሆነው ነበር፡፡ ይኸው የኩላሊት ህመም ፋታ ነስቶት በየካቲት ወር 2012 ከዚህች ዓለም አሰናብቶታል፡፡

*****

ከመግቢያዬ እንደገለጽኩት የሀገራችን የሙዚቃ አፍቃሪዎች በጣም የሚወዱት የመሐመድ ወርዲ ዘፈን “ሰበርታ” ነው፡፡ እኔም “ሱድፋ”ን ከሁሉም እንደማስበልጥ ገልጫለሁ፡፡ በሱዳኖች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነው የመሐመድ ወርዲ ዜማ ግን “ገመር ቦባ” ነው፡፡ ሱዳኖች እ.ኤ.አ. በ2000 ባደረጉት ምርጫ “አል-ገመር ቦባ” የተሰኘው ዘፈን የክፍለ ዘመኑ ምርጥ “ነጠላ ዜማ” ተብሎ ተመርጧል፡፡እኔም ገመር ቦባን በድምጽ (ኦድዮ) ልጋብዛችሁና ላብቃ፡፡

ቦባ ዐሌክ ተጊል… ቦባ ዐሌክ ተጊል

አል-ገመር ቦባ ዐሌይክ ተጊል፡፡

አስ-ሰጊሩን አል-ማ-ከቢር

አር-ሪጌበት-ጊዛዛት አሲር

አስኑን በርራጊን የሺል

አል-ዑዩን መሥለል ፈናጂል

ቢንተ-ሱዳን አሲል

ያ ገመር ቦባ ዐሌክ ተጊል፡፡

(ገመር ቦባን በዚህ ሊንክ ላይ ይስሙት https://archive.org/details/MohammedWardi-AlQamarBoeba )

——

አፈንዲ ሙተቂ

መጀመሪያ ታሕሳስ 6/2006 ተጻፈ፡፡

እንደገና ተሻሽሎ መስከረም 9/2007 ተጻፈ፡፡

The writer, Afendi Muteki, is a researcher and author of the ethnography and history of the peoples of East Ethiopia.

 You may like his facebook page and stay in touch with his articles and analysis: Just click this link to go to his facebook page.

ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ
———-                                               

ኤርትራ ዛሬ ራሷን የቻለች ሀገር ናት፡፡ ትናንት ግን የኛው አካል ነበረች፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሤ ብልጥ የሆኑ መስሎአቸው ለሁላችንም አስፈላጊ የነበረውን የፌዴሬሽን ፎርሙላ ሰረዙትና ህዝቡን አስቀየሙት፡፡ ደርግ ደግሞ የራሳችንን ህዝብ እንደ ባዕድ እየቆጠረ በመትረየስ አጨደው፡፡ በታንክ ደመሰሰው፡፡ በዚህም የተነሳ ወጣቱ “አደይ ኤሪቲሪያ”ን እየዘመረ ወደ ባርካና ሳህል ነጎደ፡፡ ራሱን አደራጅቶ ጀብሃና ሻዕቢያ ሆኖ መጣ፡፡ ውጤቱም 1983 ላይ ታየ፡፡

  

   የደርግና የኃይለ ሥላሤ መንግሥታት ያደረጓቸው ነገሮች ሲገርሙን በጣም ግራ የሚያጋባው ሶስተኛው መንግሥታችን መጣ፡፡ ይህ የኛ መንግሥት “የተበላሸውን ሁሉ አስተካክለን አብረን መኖር እንችላለን” ብሎ መከራከር ሲገባው ጭራሹኑ “ኤርትራ ካልተገነጠለች ኢትዮጵያ ሰላም አታገኝም” ባይ ሆኖ ተገኘ፡፡ ክፍለ ሀገሩ “ሓርነት ወጣ” ከተባለ በኋላ ደግሞ መንግሥቱ ከሚከተለው ግልጽነት የጎደለው አሰራር የተነሳ በ1990 ሺዎችን ያረገፈ ግዙፍ ጦርነት ተቀሰቀሰ፡፡ ከአንድ ምንጭ የተቀዱ ህዝቦች ተጋደሉ፡፡ እነሆ ዛሬም ድረስ ነገሩ ሳይለይለት በጨለማ ውስጥ ነው ያለነው፡፡

                                                               

   እኛ ግን ተስፋ አንቆርጥም! በአያያዝ ጉድለት የተለየንን ወገናችንን መመለስ እንፈልጋለን፡፡ ህዝቡ ለጊዜው ሪፈረንደም አድርጎ ነጻነቱን ማወጁን እናደግፋለን፡፡ ቢሆንም ህልም አይከለከለምና አንድ ቀን ተቀራርበን በጋራ ስለመስራት እንወያይ ይሆናል ብለን እናልማለን፡፡ የኛ ልጆች ደግሞ በኮንፌዴሬሽን ስለመስራት ያስቡ ይሆናል፡፡ የልጅ ልጆቻችን በፈቃደኝነት ስለመዋሃድ ያስቡ ይሆናል፡፡ በዚያን ጊዜም አሁን የምንመኘው በአንድነት ውብ የመሆን ሚስጢራችን ይመለስልናል ብለን እንመኛለን፡፡ ምን ይታወቃል? ለፈጣሪ የማይሳነው ነገር የለም፡፡

ወገኖቼ ደጉን ነው የተመኘሁት፡፡ በቅን ልቦና በርትተን ከጸለይንና ከኛ የሚጠበቀውን ካደረግን ሁሉንም የሚችለው ፈጣሪ ህልማችንን እውነት ያደርግልናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡

——-

   ምን እንደጣለብኝ እንጃ! ያንን ምድር እጅግ ሲበዛ እወደዋለሁ፡፡ እኔ ለተወለድኩበትና አብዛኛውን ዕድሜዬን ለጨረስኩበት የምስራቅ ኢትዮጵያ ክልል ጎረቤት ከሆነችው ሶማሊያ ይልቅ በ1600 ኪ.ሜ. የምትርቀው አስመራ ናት የምትናፍቀኝ፡፡ ስለሶማሊያ የተጻፈ መጽሐፍ ማንበብ ብዙም አይማርከኝም፡፡ ስለ ኤርትራ የተጻፈ መጽሐፍ ካጋጠመኝ ግን ሳላየው አላልፍም (ይህ ግን ሶማሊያን ከመጥላት እንደማይቆጠርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ)፡፡

    ታዲያ በርካቶቻችሁም እንደኔው ትመስሉኛላችሁ፡፡ ለምሳሌ ከ1970ዎቹ ጀምሮ ሲታተም የቆየው የቤኒ አምሩን ወጣት የሚያሳየው ፖስተር ዛሬም ድረስ ከኛ ጋር ተሳስሮ ነው ያለው፡፡ አሁንም ድረስ በበርካታ ስፍራዎች ተለጥፎ አይቼዋለሁ፡፡ በፌስቡክም እርሱን እንደ ፕሮፋይል ፒክቸር የሚጠቀም ኢትዮጵያዊ ሞልቷል፡፡ በሌላ በኩል የኤርትራን ሙዚቃ የሚያዳምጡ ሰዎች በሽ ናቸው፡፡ ደራሲ መሐመድ ሳልማን መቐለ ሄዶ ያየው ነገር ቢያስገርመው “በኤርትራ ሙዚቃ የምትጨፍር ከተማ” የሚል አስደናቂ ወግ ጽፎ እውነቱን አስረድቶናል፡፡ መንግሥታት ቢጣሉ እንኳ ህዝቦች ምንጊዜም እንደሚነፋፈቁ ከዚህ በላይ የሚያስረዳ ዋቢ ያለ አይመስለኝም፡፡

——–

     ማርታ ሀይሉን አስታወሳችኋት? አዎን! ማርታን “ብራ… ነው… ብራ ነው”፤ “አዘዞ”፤ “ሎጋ ..ና እናውጋ” በተሰኙት ዘፈኖቿ እናውቃታለን፡፡ ከማርታ ዘፈኖች ዘወትር ቀልቤን ይገዛ የነበረው ግን የትግርኛ ዜማዋ ነው፡፡ አዝማቹ እንዲህ ይመስለኛል፡፡

 ካብ አስመራ ድንገት ርእዮ

ምጽዋ ገባሁ ልበይ ሕብዮ፡፡

እንተርጉመው እንዴ?… ግድ የለም ማርታ ራሷ እንዲህ እያለች በአማርኛ ተርጉማዋለች፡፡

“ከአስመራ ድንገት አይቼው

ምጽዋ ገባሁ ልቤን ሰጥቼው”፡፡

     አዎን! ትናንት የኛ ናት ስንላት ለነበረችው ኤርትራ ነው እንዲህ የዘመርንላት፡፡ ዛሬም ብንዘምርላት እንከበራለን እንጂ አንወቀስም፡፡ ምክንያቱም በመንግሥት ደረጃ ነው የተለያየነው፡፡ ሁለት ፓስፖርት እንዲኖረን ነው የተደረግነው፡፡ ሁለታችንም ግን አንድ ህዝቦች ነን፡፡ በደምም ሆነ በባህል በጣም የተዋሃድን የአንድ መሬት ብቃዮች ነን፡፡ ሁለታችንም የተዋብን የሴምና የኩሽ ህዝቦች ውቅር ነን፡፡ እንደኛ የሚያምር ህዝብ በትኛውም ዓለም የለም፡፡ የጀበና ቡና፣ ዶሮ ወጥ፣ ድፎ ዳቦ፣ የስጋ ፍትፍት፣ አምባሻ፣ ወዘተ…. ሁለታችን  ዘንድ ብቻ ነው ያለው፡፡

—–

    በርግጥ እላችኋለሁ፡፡  በምንባብና በወሬ እንጂ በአካል የማላውቃት ኤርትራ ትናፍቀኛለች! ያ በታሪክ ምዕራፎች “ምድሪ ባህረ ነጋሽ” እየተባለ ሲጠራ የኖረው ጀግና መሬትና ህዝብ ይናፍቀኛል፡፡ ያ የሰሜኑ በረኛ እያልን ስንመካበት የነበረው ህዝባችን ይናፍቃል፡፡

እውነትም ኤርትራ ! የዳማት ታሪክ ውቅር! የመጠራ አብያተ መንግሥታት ከርስ! የሀውልቲ ፍርስራሾች ቀብር! የአዱሊስና የዙላ ወደቦች መዘክር! የሱዋኪምና የዳህላክ ሱልጣኖች ደብር!

ኤርትራ የአብረሃ ደቦጭ ሀገር! የሞገሥ አስገዶም ሀገር! የዘርዓይ ደረስ ሀገር! የሎሬንዞ ታዕዛዝ ሀገር! የደጃች ሀረጎት ሀገር! በአይበገሬ ጀግንነታቸው ድፍን አፍሪቃን ያኮሩ አርበኞች የበቀሉበት ምድር!

ኤርትራ የበረከት መንግሥተ አብ ሀገር! የፀሐይቱ ባራኪ ሀገር! የአብረሃም አፈወርቂ ሀገር! የአሕመድ ሼኽ ሀገር! የሄለን መለስ ሀገር! የየማነ ባሪያው ሀገር! የሄለን ጳውሎስ ሀገር! በስርቅርቅ ድምጻቸው የሰውን ልብ እየሰረሰሩ የመግባት ሀይል ያላቸው የጥበብ ከዋክብት የወጡበት መንደር!

ኤርትራ የፊያሜታ ጊላይ ሀገር! የስዕላይ በራኺ ሀገር! የኦቦይ ተኽሌ ሀገር! የተክላይ ዘድንግል ሀገር! የሆቴል ፓራዲዞ ሀገር! የዕቁባይ ሲላ ሀገር! የምንወደው ደራሲያችን በዓሉ ግርማ በ“ኦሮማይ” መጽሐፉ እንደ ፊልም ግልጥልጥ አድርጎ እየተረከልን ዝንተ-ዓለም እንድንወዳት ያደረገን የቀይ ኮከብ ትዝታ ወመዘክር!

ኤርትራ የፊዮሪ ሀገር! የሳባ ሀገር! የማርቲና ሀገር! የብርኽቲ ሀገር! ፊያሜታ ጊላይን የመሳሰሉ “ሽኮሪናዎች”ን ያበቀለች ውብ የውቦች እመቤት!

—–

  ኤርትራን ስንጠራ በቅድሚያ ወደ አዕምሮአችን የምትመጣው አስመራ ናት፡፡ የአስመራ ናፍቆት ይገድላል፡፡ አስመሪና፣ አስመሪቲ፣ አቲ ጽብቕቲ!…

ውይ ስታምር! “ቀሽቲ” እኮ ናት፡፡ ያኔ በልጅ አዕምሮአችን በዘምባባ ጥላዋ ተሸክፋ በፖስትካርድ ስትቀርብልን “የኛ ውቢት” እያልን እንመጻደቅባት ነበር፡፡ እንቆቅልሽ ስንጫወትና መልሱ ጠፍቶን “ሀገር ስጠኝ” ስንባል እርሷን ለመስጠት እንሰስት ነበር፡፡ ጠያቂውም የዋዘ ስላልሆነ “አስመራ” ካላልነው ለጠየቀን ጥያቄ ትክክለኛውን መልስ አይነግረንም ነበር፡፡ ከማናውቃቸው “ዋሽንግተን” እና ሮማ ይልቅ አስመራ ነበር የምትበልጥብን፡፡ በትምህርት ቤት መዝሙራችንም እንዲህ እንል ነበር፡፡

ኦኬ ኦኬ ኦኬ ስራ

ሰላም ሰላም ወደ አስመራ

አዲስ አስተማሪ ከጃፓን የመጣ

ማስተማሩን ትቶ በቦክስ የሚማታ

አናግረኝና አናግርሃለሁ

በአሜሪካ ሽጉጥ አዳፍንሃለሁ፡፡

አማርኛም አልችል ትግርኛም አልሰማ

ሰተት ብዬ ልግባ አስመራ ከተማ፡፡

ግጥሙ “አንታራም” የሚሉት የህጻናት ጨዋታ ዓይነት ነው፡፡ ነገር ግን አስመራ ከልባችን እንዳትጠፋ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ዛሬም በልባችን ነግሳለች አስመሪና!

 —-

አስመሪና! እቲ ሽኮሪና! ሰሜናይት ጽብቕቲ! በዓሉ ግርማ ላንቺ ክብር የጻፈው ትዝ ይልሻል? እስቲ እናስታውሰው!

አስመሪና አስመራዬ

ካብ ሐንቲ ንግሥቲ ይበልፅ መልክእኪ

አማአድዬ ክርእየኪ ከሎኹ ኽአ

አብ ኢደይ ዘሎ ነገር ይወድቕ፡፡

(አስመራ አስመራዬ)

(ከአንድ ንግሥት ይበልጣል መልክሽ)

(በሩቅ ሲያይሽ በውበቷ ስለተማረሽ)

በእጄ ያለ ነገር ሳይታወቀኝ ይወድቃል)

——

  ጸጸራት፤ ፎርቶ፣ ሐዝሐዝ፣ አርበእተ አስመራ፣ እምባጋሊያኖ፣ ኮምቢሽታቶ፣ አዲ ጓእዳድ፣ ቃኘው፣ ማይተመናይ፣ ሰምበላይ፣ ጎዳይፍ፣  ገጀረት፣ ወዘተ… በጽሑፍ የማውቃቸው የአስመራ ሰፈሮች ናቸው፡፡ አንድ ቀን በሆነልኝና ባየኋቸው እያልኩ አልማሁ፡፡  እነዚህ አስገራሚ የአስመሪና ሰፈሮች ብዙ ባለታሪኮችን አብቅለዋል፡፡ ብዙዎች ገድላቸው እየተደጋገመ ሲነገርላቸው እሰማለሁ፤ አነባለሁ፡፡ ለኛ ቅርብ የነበረ አንድ ውድ ልጅ እየተረሳ በመሆኑ ግን አዝኛለሁ፡፡

 

     አማኑኤል እያሱ ይባላል! አስታወሳችሁት አይደል? አዎን! አማኑኤል በኛ ዕድሜ ዘመን ኢትዮጵያ ዋንጫ መብላት እንደምትችል ያስመሰከረው የታላቁ የ1980 የእግር ኳስ ቡድናችን ቋሚ ተሰላፊ ነበረ፡፡ የማሊያ ቁጥሩ 2 ይመስለኛል፡፡ አማኑኤል የያኔው ቡድናችን ባደረጋቸው ሁሉም ጨዋታዎች ተሰልፏል፡፡ ቡድኑ ዋንጫውን ሲበላም ከጓደኞቹ ጋር ቤተመንግሥት ድረስ ተጋብዞ ተሸልሟል፡፡ አማኑኤልን ያስገኘው ከዚያ ዘመን ዝነኛ ቡድኖቻችን መካከል አንዱ የነበረው የኤርትራ ጫማ ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን የኤርትራ አንደኛ ዲቪዚዮን ዋንጫን በተደጋጋሚ ያሸነፈ ነው፡፡

 

    አማኑኤል እያሱ በኢትዮጵያ ትቅደም አንደኛ ደረጃ ዋንጫም ለኤርትራ ክፍለ ሀገር ምርጥ ቡድንም ተሰልፎ ተጫውቷል፡፡ ባልሳሳት የ1981 የኢትዮጵያ ዋንጫን ያሸነፈው እነ አማኑኤል የነበሩበት የኤርትራ ክፍለ ሀገር ቡድን ነው፡፡ የአማኑኤል እያሱን ወሬ ለመጨረሻ ጊዜ ያነበብኩት በ1988 ለወዳጅነት ጨዋታ አዲስ አበባ መምጣቱን በማስመልከት በርካታ የግል ጋዜጦች ቃለ-መጠይቅ ባደረጉለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ መረጃው የለኝም፡፡ እስቲ የአስመራ ልጆች ወሬው ካላችሁ ስለአማኑኤል እያሱ አንድ ነገር በሉን፡፡

—————–

አሁን ወደ ምዕራብ ኤርትራ ተሻግረናል! ባርካና ጋሽ የሚባሉት ቆላማ አውራጃዎች እዚህ ነው ያሉት፡፡ አቆርዳት፣ ተሰነይ፣ አሊጊደር፣ ኡምሐጀር፣ ባሬንቱ የተሰኙት ከተሞች በቆላው ምድር ውስጥ ተዘርግተዋል፡፡ ኩናማ፣ ናራ እና ቤጃ የሚባሉት ብሄረሰቦች እዚህ ነው የሚኖሩት፡፡ የአካባቢው ዋነኛው ህዝብ ግን ለኛ በጣም ቅርብ የሆነውን ሳቂታውን የቤኒ አምር ወጣት ያስገኘው የትግረ ህዝብ ነው፡፡

  የትግረ ህዝብ በውስጡ በርካታ ጎሳዎች አሉት፡፡ ከሁሉም የሚበረክተው ግን የቤኒ አምር ጎሳ ነው፡፡ ህዝቡ የሚነጋገርበት የትግረ ቋንቋ ከሴማዊ ቤተሰብ ነው የሚመደበው፡፡ ለዚህ ቋንቋ በጣም የሚቀርበው በደጋው ኤርትራና በኛዋ የትግራይ ክልል የሚነገረው ትግርኛ ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ቋንቋዎች ከጥንታዊው የግዕዝ ቋንቋ ነው የተወለዱት፡፡ የትግረ ቋንቋን ከ35 በመቶ የማያንሰው የኤርትራ ህዝብ ይናገረዋል፡፡ “ትግረ” ከኤርትራ ሌላ በሱዳንም (ከሰላ አካባቢ) በስፋት ይነገራል፡፡

ትግረና ትግርኛ በጣም ከመመሳሰላቸው የተነሳ እንግዳ ለሆነ ሰው አንድ ዓይነት ቋንቋዎች ሊመስሉት ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም ለትግርኛ ተናጋሪዎች የትግረ ቋንቋን መልመድ በጣም ቀላል ነው ይባላል፡፡ የትግረ ተናጋሪም ትግርኛን በቶሎ መልመድ ይቀለዋል፡፡ በመሆኑም ከጠቅላላው የኤርትራ ህዝብ 50% የሚሆነው ሁለቱንም ቋንቋዎች መናገር ይችላል (ይህ ቁጥር ትግርኛ ብቻ የሚናገሩትን፣ ወይንም “ትግረ” ብቻ የሚናገሩትን አይጨምርም)፡፡

 ምዕራባዊው ቆላ ኤርትራዊያን በጣም የሚያደንቋቸውን እንደ ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ፣ ሙሐመድ ኢድሪስ እና ኢድሪስ ገላውዴዎስን ያፈራ መሬት ነው፡፡ በዚህ ሰሞን ልቤን ያሸፈተው የትግረ ልጅ ግን “አሕመድ ሼክ” ነው፡፡ አሕመድ ሼክን አወቃችሁት አይደል? አዎን! “ባቡሬይ”፣ “ኢላ ሰርጎ” ወዘተ.. እያለ በማይጠገበው የትግረ ምት የሚያዜመው ተወዳጅ ድምጻዊ ነው፡፡ አንድ ኤርትራዊ ወዳጃችን “ኤላ ሰርጎ”ን ሲፈታልን `ከጀርባው ፌሎሶፊ አለው” ነው ያለኝ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡

 

   የትግረ ሴት ለምትወደው አንድ ሰው (ለባሏ) እንጂ ለማንም ጸጉሯን አትገልጠውም፡፡ ስለዚህ ጉብሊቷን ልጅ የወደደው አሕመድ ሼክ በተዋቡ ግጥሞች እያወደሳት ዘፈነላትና ፍቅሩ ልቧ ውስጥ ዘልቆ መግባቱን ለማረጋገጥ ጸጉሯን ማየት ጀመረ፡፡ እርሷም ግጥሞቹን ከሰማችለት በኋላ ጸጉሯን ገልጣ አሳየችው፡፡ ድል አድራጊው ወዲ ሼክም ይዟት በረረ፡፡ “ኤላ ሰርጎ! ኤላ ሰርጎ” እያለ ነጎደ!

——

ሰሜን ኤርትራ!

ተወዳጇ የከረን ከተማ እዚህ ነው ያለችው! የሀረርጌዋ የድሬ ዳዋ ከተማ መንትያ እህት የምትመስለው ውቢቷ የሰሜን ፈርጥ! በቪዲዮ አይቻት ውበቷን አደነቅኩላት! አበቦቹ! ቤቶቹ! መንገዶቹ ሁሉም ውብ ናቸው፡፡ ከትግራይ የተገኘው ዝነኛው ብርሃነ ሃይለ አንድ ላይ በነበርነበት ዘመን ለከረኗ ጉብል እንዲህ ብሎላታል፡፡

ሸው በሊ ብለነይ ብለነይ

ዝለሊ ብለነይ ብለነይ

አሊሊ ብለነይ ብለነይ

አቲ ጓል ከረነይ ብለነይ

አዎን! ቢለን ከከረን ከተማ ጋር ስሙ የሚጠቀስ ብሄረሰብ ነው፡፡ ቋንቋው ከኛው የአገው ቋንቋ ጋር አንድ ዐይነት ነው፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ነው አንባቢ ሊመራመር የሚገባው፡፡ በወሎና በጎጃም የሚኖረው አገው ምን ሊያደርግ እዚያ ሄደ?… መቼ ነው እዚያ የሄደው?… መላምት ከመዘብዘብ በስተቀር ማንም ሰው ይህንን እንቆቅልሽ በሚያመረቃ ሁኔታ ሊፈታው አልቻለም፡፡ ኤርትራና እኛ አንድ ነን የሚያሰኘኝ እንዲህ ዓይነት ተጨባጭ ማስረጃ ስላለን ነው፡፡

  

  ቢለን ውብ ባህል ያለው ህዝብ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ሴቶቹ ካገቡ በኋላ ጸጉራቸውን መሰተር ግድ ነው፡፡ ህዝቡ የቢለን ቋንቋ ተናጋሪ ቢሆንም የትግረ ቋንቋንም ይጠቀማል፡፡ ትግርኛም በስፋት ይነገራል፡፡ በጣም ታዋቂ የሆነው የቢለን ተወላጅ “ዑመር እዛዝ” ነው፡፡ የጀብሃ ጦር ከመፍረክረኩ በፊት የሁለተኛው ዞን አዛዥ እንደነበረ ከዚህ በፊት ጽፌ ነበር፡፡

  ከከረን ሽቅብ ወደ ሰሜን ስናመራ ታሪካዊቷ አፋቤት አለች፡፡ ጄኔራል ታሪኩ አይኔ የሚመራው ናደው እዝ እዚህ ነበር የሰፈረው፡፡ የቀይ ኮከብ ዘመቻ ዋና አምባም ይህ ነበር፡፡ ከአፋቤት ወደ ሰሜን ስንበር ንዳዳማውና አስቸጋሪው የሳህል መሬት አለ፡፡ በሳህል እምብርት ላይ የኤርትራ ገንዘብ መጠሪያ ለመሆን የበቃችው “ናቅፋ” አለች፡፡ በዓሉ ግርማ እንደተረከልን ከሆነ ሳህል ማለት እሳት ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ይኖሩበታል፡፡ ከብቶች ይሰማሩበታል፡፡ ተክልም ይበቅልበታል፡፡ እዚህ አካባቢ በብዛት የሚኖረው ህዝብ “ረሺዳ” ይባላል (አንዳንዶች “ራሻይዳ” ይሉታል፤ ስህተት ነው፤ ትክክለኛው አጠራር “ረሺዳ” ነው)፡፡

  የ“ረሺዳ” ህዝብ ከሌላው የኤርትራ ህዝብ የሚለይበት በርካታ ነገሮች አሉት፡፡ ለምሳሌ ይህ ህዝብ ከሳዑዲ ዐረቢያ ተነስቶ ወደ ኤርትራ የገባው በቅርብ ዘመን (በ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ) ነው፡፡ በዚያ ወቅት የአሁኗ ሳዑዲ ዐረቢያ አልነበረችም፡፡ ሀገሩ ሁሉ በጎሳዎች የተከፋፈለ በረሃማ ምድር ነበር፡፡ ከነዚህ ጎሳዎች አንዱ አል-ረሺድ ይባላል፡፡ ይህ የአል-ረሺድ ህዝብ የአካባቢው የበላይ እንዲሆን በኦቶማን ቱርክ ተወሰነ፡፡ አብዛኛው ህዝብም ለነርሱ አደረ፡፡ “አል-ሱዑድ” የሚባለው ቤተሰብ ግን “አሻፈረኝ” አለ፡፡ “ራሴ በረሃውን ጠቅልዬ መግዛት ስችል ለምን በአል-ረሺድ ጎሳ የበላይነት አድራለሁ” በማለት አንገራገረ፡፡ በሁለቱ መካከል ጠብ ተነሳ፡፡ በመጀመሪያው ላይ የአል-ረሺድ ጎሳ አሸነፈ፡፡ አል-ሱዑዲዎች ወደ ኢራቅ ሸሹ፡፡

   ከጥቂት ዓመታት በኋላ ግን የአል-ሱዑድ ቤተሰብ በእንግሊዞች ደጋፊነት ራሱን አጠናክሮ መጣ፡፡ በአል-ረሺድ ጎሳ ላይም ድልን ተቀዳጀ፡፡ በዚህም የተነሳ የዐረቢያ በረሃ ለአል-ረሺድ ጎሳ አባላት ሲኦል ሆነ፡፡ ረሺዳዎች እየተያዙ በጅምላ ታረዱ፡፡ ንብረታቸው ተዘረፈ፡፡ በፊት ይረዳቸው የነበረው የቱርኮች መንግሥት በራሱ ችግር በመወጠሩ ምንም ሊያደርግላቸው አልቻለም፡፡ በመሆኑም ከእልቂቱ ለመዳን ሲሉ ባህር እያቋረጡ ወደ አፍሪቃ ምድር ተሰደዱ፡፡ በሱዳንና በኤርትራ መኖሪያቸውን ቀለሱ፡፡

እንግዲህ ረሺዳዎች ከዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሸሽ ወደ ኤርትራ የመጡ ተፈናቃዮች ናቸው ማለት ነው፡፡ በኤርትራ ውስጥ ንጹህ የዐረብ ዝሪያ የሚባሉት እነርሱ ናቸው፡፡ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸውም ዐረብኛ ነው፡፡ በዚህ ህዝብ ባህል መሰረት ለአካለ መጠን የደረሰች ማንኛዋም ሴት ፊቷንም ሆነ ጸጉሯን መሸፈን ግዴታዋ ነው፡፡ በዓሉ ግርማ በኦሮማይ ውስጥ ሲተርክልን “ማንኛውም የረሺዳ ባል የሚስቱን ፊት ገልጦ የሚያይበትን ሰው አይፈልግም” በማለት የተናገረውም የባህላቸው አንድ አካል ነው፡፡

——-

አሁን ወደ ምስራቅ ኤርትራ ተሻግረናል፡፡ ብርኽቲ የሆነችው ምጽዋ እዚህ ነው ያለችው፡፡ ብርሃነ ሃይለ “ሸው በሊ ብለነይ” የተሰኘውን ዘፈን ሲቀጥል ምጽዋን እንዲህ ይላታል፡፡

“አብ ዋሊድ ማሳዋ

ኩለ ሊየን ሒልዋ”

 

   ትርጉሙን በትክክል ባላውቀውም “የምጽዋ ልጆች ሁሉም ጣፋጭ ናቸው” የሚል መልዕክት እንዳዘለ ይገባኛል፡፡ የምጽዋ ልጆች ቆንጆ ናቸው ተብሎ እየተደጋገመ ተነግሮላቸዋል፡፡ ከወደብ ከተማ የተገኙ በመሆናቸው ዓለም አቀፍ ስልጣኔና ልዩ ልዩ ባህሎች በነርሱ ላይ ሲነፍስ ይታያል፡፡

  ምጽዋ በጣም ውብ ናት፡፡ በተለይም ኪነ-ህንጻዋ ብዙ ተብሎለታል፡፡ ከዑስማናዊያን ቱርኮች ዘመን ጀምሮ ብዙ ገዥዎች ሲፈራረቁባት የነበረች መሆኗ በከተማዋ የሚታየውን ኪነ-ህንጻ እንዳሳመረው ምሁራን ያስረዳሉ፡፡

  

ኤርትራዊያን ምጽዋን ይወዷታል፡፡ እኛም እንወዳታለን፡፡ ነገር ግን ወደዚያ ለመድረስ የሚሻ ሰው እንደ እሳት የሚፋጀውን ሙቀቷን መቻል አለበት-ከተማዋ በዓለም ላይ ከፍተኛ ሙቀት ካላቸው ስፍራቸው አንዷ ናትና፡፡ የዚህች ከተማ ህዝብ ኑሮውን ከአየር ጸባዩ ጋር እንዲጣጣም አድርጎ ቀይሶታል፡፡ በመሆኑም አብዛኛው የንግድ እንቅስቃሴ የሚከናወነው ከምሽት እስከ እኩለ ሌሊት ባለው ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ከተማዋ ለዘወትር እንደጋለች አትቀርም፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ሙቀቱ ጋብ ይልና ጤናማው አየር ይነፍስባታል፡፡ ይህም ከጥር-የካቲት ባለው ጊዜ እና በሀምሌ ወር ነው፡፡ በነዚህ ወራት ከተማዋን የሚጎበኘው ቱሪስት በጣም ይጨምራል፡፡ በቀድሞው ዘመን ቀዳማዊ ኃይለሥላሤም ከተማዋን ለመጎብኘት የሚመጡት በነዚህ ወራት ነው (እርሳቸው ያሰሩት ቤተ-መንግሥት እስከ አሁን ድረስ አለ)፡፡

     ምጽዋ በወደብነት አገልግሎት መስጠት የጀመረችበት ዘመን በትክክል አይታወቅም፡፡ የታሪክ ምሁራን እንደሚሉት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በአካባቢው ከተማ ቀመስ ሰፈራ ነበር፡፡ ይሁንና እስከ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እንደ ወደብ ሲያገለግሉ የነበሩት ከምጽዋ አጠገብ የነበሩት ጥንታዊያኑ “ዙላ” እና “አዱሊስ” ነበሩ፡፡ የምጽዋ ተፈላጊነት ጉልህ ሆኖ የተከሰተው የባህር መደቡ በ1508 በዑሥማናዊያን ቱርኮች (Ottoman Turks) በተያዘበት ወቅት ነው፡፡ ከቱርኮቹ በማስከተልም ግብጾችና የኢጣሊያ ወራሪዎች ተፈራርቀውባታል፡፡

   ኢትዮጵያና ኤርትራ በፌዴሬሽን ከተዋሃዱ በኋላ ምጽዋ ከፍተኛ እመርታ ማሳየት ጀምራ ነበር፡፡ ከ1970ዎቹ መግቢያ ጀምሮ ግን የጦርነት ቀጣና ሆነች፡፡ የሻዕቢያ ሀይሎችና የኢትዮጵያ ሰራዊት ከፍተኛ እልቂት የተፈጸመባቸውን ጦርነቶች አካሂደውባታል፡፡ በተለይም በ1982 (እ.ኤ.አ. 1990) በተካሄደው ጦርነት ከሁለቱም ወገን በአስር ሺህ የሚቆጠር ሰራዊት መርገፉን ሁኔታውን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖችና የዐይን ምስክሮች ገልጸዋል (የሀምሳ አለቃ ታደሰ ቴሌ ሳልባኖን “አይ ምጽዋ” አስታውሱት)፡፡ የቀድሞው የኢትዮጵያ መሪ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያምም “ለከፍተኛ ሽንፈትና ኪሳራ የዳረገን ውድቀት ያጋጠመን በምጽዋ ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

የድሮው ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) የአሁኑ “ህዝባዊ ግንባር ንዴሞክራሲን ንፍትሒን” (ህግዴፍ) ምጽዋን የተቆጣጠረበትን ዘመቻ “ኦፕሬሽን ፈንቅል” በማለት ይጠራዋል፡፡ ምጽዋ የተያዘችበት ዕለትም (የካቲት 20) በየዓመቱ ይከበራል፡፡ በርካታ ህዝብ ወደ ምጽዋ ከሚጎርፉባቸው ዕለታት መካከልም አንዱ ይህ “የኦፕሬሽን ፈንቅል” መታሰቢያ የሚከበርበት ቀን ነው፡፡

ምጽዋ የብዙ ህዝቦች መኖሪያ ናት፡፡ ዋነኞቹ ነ&#48

ጸሐፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ

ዛሬም በበረሃውና በቆላው ክልል የምናደርገውን የኢትኖግራፊ ጉዞ ቀጥለናል፡፡ የተአምረኛውን እንስሳ አስገራሚ ባህሪዎችና ታሪካዊ ገድሎች የተቻለንን ያህል እንጨዋወታለን፡፡

*****

ግመል ያመነዥካል፡፡ ነገር ግን ከሌሎች አመንዣኪ የቤት እንስሳት በብዙ መልኩ ይለያል፡፡ ለምሳሌ የግመል የእግር መዳፍ እንደሌሎች እንስሳት ለሁለት የተከፈለ ቢሆንም በእግሩ ላይ ሽኮና የለውም፡፡ በሽኮናው ፋንታ ሁለቱ የመዳፉ ክፍሎች ጠንከር ባለ ቆዳ የተሸፈነ ነው፡፡  በመዳፉ ላይ ያለው ቆዳ በጉዞ ወቅት ይዘረጋል፡፡ በመሆኑም በጸሐይ ሙቀት የሚግለው የበረሃ አሸዋ እግሩን እያቃጠለ አያሰቃየውም፡፡ በተጨማሪም ቆዳው የበረሃ አሸዋና ኮረኮንች በመዳፉ ውስጥ እንዳይገባበት ይከላከልለታል፡፡

በግመል ዐይን ላይ ያለው ድርብ ሽፋን በበረሃ ውሽንፍርና ማዕበል የሚበተነው አሸዋ በዐይኖቹ ውስጥ እንዳይገባበት ይከላከላል፡፡ በደረቱ ላይ ያለው ወፍራም ፍርምባ መሰል አካል እና በጉልበቶቹ ላይ ያሉት ጠንካራ የቆዳ ሽፋኖች ግመሉ በሚተኛበት ወቅት አሸዋው እንዳያቃጥለው ይረዱታል፡፡ ታዲያ እንስሳው በብርድ ወራትም በቆፈን እንዳይጠቃ የሚረዳው ጸጉር በተፈጥሮ ተሰጥቶታል፡፡ ብርዱ እየበረታ ሲመጣ ጸጉሩ በጣም ያድጋል፡፡ ብርዱ ካለፈ በኋላ ግን ጸጉሩ ወይ በባለቤቶቹ ይቆረጣል፤ አሊያም በሙቀት ሀይል እየተቀረፈ ይወድቃል፡፡

 “እንደ ግመል ሽንት ወደ ኋላ” ሲባል ሰምታችኋል አይደለም… አዎን! ግመል ሽንቱን ወደ ኋላ ነው የሚለቀው፡፡ ፋንድያውንም ወደ ኋላ ነው የሚበትነው፡፡ የፋንድያው የእርጥበት ይዘት በጣም አነስተኛ በመሆኑ በጥቂት ጊዜ ውስጥ ለማገዶነት ማዋል ይቻላል፡፡ የግመል ወተት በማዕድናት እና በብረት ይዘቱ ከሌላው ወተት ይበልጣል፡፡ ቆለኞችና የበረሃ ሰዎች ወተቱን እንደ ምግብም እንደ ውሃም ይጠቀሙበታል፡፡ ስጋው ደግሞ ቅባት የሌለው በመሆኑ ለጤና ተስማሚ ነው፡፡ ከዚህም በላይ እንስሳው ልዩ ልዩ ተክሎችን የሚበላ በመሆኑ ስጋው መድኃኒትነት ያለው መሆኑ ተረጋግጧል (የሀገራችን አርብቶ አደሮች ግመል “ሀሞት” የለውም በማለት ያምናሉ፤ በመሆኑም ስጋው ከበሽታ የጠራ ነው ይላሉ)፡፡

ግመል ሲታረድስ አይታችኋልን!! … ግመሉ ሰታረድ ይንበረከካል እንጂ እንደ ከብትና ፍየል እግሮቹ በገመድ ተጠልፈው መሬት ላይ አይጣሉም፡፡ ግመሉ በእንብርክኩ ከተቀመጠ በኋላ አንገቱ በገመድ ወደ ኋላ ይታሰራል፡፡ ከዚያም ቢላዋው በታችኛው የአንገቱ ክፍል ይገዘገዝበታል፡፡ ታዲያ ግመል በሚታረድበት ወቅት ቢላዋውን እንዲያይ አይደረግም፡፡ እንስሳው ቢላዋ ካየ እንባውን እየዘራ ያለቅሳል ይባላል፡፡ ስለዚህ ቆለኞች ምንም ጊዜም ቢሆን ለግመል ቢላዋ አያሳዩም፡፡    

*****

ግመል ከወተትና ከስጋው በላይ በመጓጓዣነቱ በሚሰጠው አገልግሎት ነው የሚታወቀው፡፡ ለብዙ ሺህ ዘመናት በረሃውን እያቆራረጠ ሰዎችን አገልግሏል፡፡ የጥንቱ ሲራራ ነጋዴዎች (Caravan Traders) ንግድን ሊያስፋፉ የቻሉት በግመል ታግዘው ነው፡፡ ይህ እንስሳ በአንድ ጊዜ እስከ አምስት መቶ ኩንታል መሸከም ይችላል፡፡ ዕቃው ተጭኖበት ምንም ዐይነት የድካም ስሜት ሳይታይበት ለብዙ ኪሎሜትሮች ይጓዛል (ግመል በአንድ ቀን እስከ 160 ኪሎሜትር ያህል መጓዝ ይችላል)፡፡

 

  ታዲያ ግመል እንደ ሌሎች እንስሳት በቁሙ አይደለም ሸክሙን የሚሸከመው፡፡ ሰውም ሆነ ዕቃ ሲጫንበት በርከክ ብሎ መሬት ላይ ይቀመጣል፡፡ ዕቃው ከተጫነበት በኋላ ያለ ምንም ችግር ተነስቶ ይቆማል፡፡ ግመል በጉዞውም ይለያል፡፡ እቃ ተጭኖበትም ሆነ ባዶውን ሲጓዝ በአንድ ጎን ያሉትን እግሮቹን አንድ ላይ ያነሳል፡፡ በመሆኑም የበረሃውን ጉዞ በቀላሉ ይወጣዋል፡፡ ለግመል በአሸዋ ውስጥ መጓዝ  በውሃ ውስጥ የመዋኘትን ያህል ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ሌሎች እንስሳት በጉዞ ወቅት በአንድ በኩል ያለውን የፊት እግርና በሌላው በኩል ያለውን የኋላ እግር ነው አንድ ላይ የሚያነሱት)፡፡ ግመል ከሁሉም በላይ የሚታወቅበት ባህሪው በገመድ አንድ ላይ ተቀጣጥሎ ለመጓዝ መቻሉ ነው፡፡ እስከ ሀምሳ የሚሆኑ ግመሎችን አንዱን በአንዱ ጭራ ላይ በገመድ አስሮ እንደ ኮንቮይ ማግተልተል ይቻላል፡፡  

ግመል በአንዳንድ ቆላማ ስፍራዎች ከዚህም የተለየ አገልግሎትም ይሰጣል፡፡ ለምሳሌ የሀገራችን ትልቁ በረሃ በሆነው የኦጋዴን ክልል የሚኖሩ የሶማሊ ቆለኛ ወገኖቻችን ግመሉን እንደ በሬ ያጠምዱትና እርሻቸውን ያርሱበታል፡፡ በትግራይ፣ በሱዳን እና በኤርትራ የሚኖሩ ቆለኞች ደግሞ በግመል እየተጠቀሙ ዘይት ይጨምቁበታል፡፡ እንዲሁም ግመሉን የወፍጮ ድንጋይ እንዲዘውር ያደርጉታል፡፡በሰሃራ እና በሌሎች በረሃዎች ደግሞ በረኸኞቹ በግመል ሀይል እየተጠቀሙ ከጥልቅ ጉድጓዶች ውሃ ይቀዳሉ፡፡      

  ግመል በሚዳራበት ሁኔታም ከሌሎች እንስሳት ይለያል፡፡ ኮርማውና ሴቷ ግመል ግንኙነት በሚፈጽሙት ወቅት ወደ ኋላ ዞረው ይተኛሉ፡፡ ሩካቤውን ለመፈጸም ግን የሰዎች እርዳታ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ታዲያ በሀገራችን አርብቶ አደሮች ባህል መሰረት ግመሎች ሩካቤ በሚፈጽሙበት ወቅት በስፍራው የሚገኙት ሴቶች እንጂ ወንዶች አይደሉም፡፡ ግመሎቹን ወንድ ልጆች ካዩዋቸው በጣም ይቆጣሉ ይባላል፡፡

ግመል ከሰዎች ጋር በበጎ ሁኔታ እንደሚኖረው ሁሉ በመቆጣትና ቂም በመቋጠርም አንደኛ ነው፡፡ በተቆጣ ጊዜ ሰዎችን በጥርሱ ነካክሶ ሊገድል ይችላል፡፡ በእግሮቹም ደፍጥጦ አደጋ ያደርሳል፡፡ በጣም አደገኛ እርምጃው ደግሞ በፍርምባው የሚያስከትለው ጉዳት ነው፡፡ በተለይ ቂም የያዘበትን ሰው አዘናግቶ ይጥለውና በፍርምባው ተኝቶበት ይገድለዋል ሲባል ሰምቻለው፡፡ አንድ ሰው ግመሉ ከሚያደርሰው አደጋ ለመዳን ለፈለገ ልዩ ልዩ ዘዴዎችን መጠቀም አለበት፡፡ ለምሳሌ ሰውዬው ግመሉ መቆጣቱን ሲያይ የቁልቁለት አቅጣጫ ይፈልግና ለትንሽ ጊዜ ይሸሸዋል፡፡ ግመሉ ሰውዬውን በእልህ ማባረር ሲጀምር ሰውዬው ወደ ግራው ወይንም ወደ ቀኝ እጥፍ ብሎ ጉዞውን ይቀጥላል፡፡ ግመሉ ራሱን መቆጣጠር ስለማይችል ወደ ጎን ሳይታጠፍ የቁልቁለት ሩጫውን ያስነካዋል፡፡ በዚህ ዘዴም ሰውዬው ከአደጋው ተረፈ ማለት ነው፡፡ በሌላ በኩል ግመል የተቆጣው ሰው ሸሚዙን አውልቆ ከፊቱ ቢጥልለት አደጋውን ሊቀለብስ ይችላል ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ “ግመሉ ሰውዬውን ያገኘ መስሎት ሸሚዙን ባለ በሌላ ኃይሉ ይረጋግጠውና ንዴቱን በርሱ ላይ ይወጣል”-ይላሉ የቆላ ሰዎች፡፡

 *****

ግመል ለብዙ ዘመናት ከሰዎች ጋር ከመኖሩ የተነሳ በስነ-ቃል ውስጥ በሰፊው ይጠቀሳል፡፡ ግመልን በመመርኮዝ የተፈጠሩ ብዙ  ተረቶች፣ ምሳሌዎችና አፈታሪኮች አሉ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እየሱስ ክርስቶስ “ሃብታም መንግሥተ ሰማያትን ከሚወርስ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል” ማለቱ ተጠቅሷል፡፡ በቅዱስ ቁርአን ውስጥም “እነዚያ በአላህ አንቀጾች ያስተባበሉት ግመል በመርፌ ቀደዳ እስኪያልፍ ድረስ ገነትን አይገቧትም” የሚል “አያት” (አንቀጽ) አለ፡፡ ነቢያትና ሌሎች ታላላቅ ሰዎች በግመል ተጓጉዘዋል፡፡ አንዳንድ ዝነኛ ሰዎች ደግሞ ስማቸው ከግመል ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለምሳሌ የነብዩ ሙሐመድ ባልደረባና የመጀመሪያው ኸሊፋ የሆኑት አቡበከር ትክክለኛ ስማቸው “አቢ ቁሃፋ” ነበር፡፡ “አቡ በከር” የሚለው ስም የተሰጣቸው “በከር” የምትባል ተወዳጅ ሴት ግመል ስለነበረቻቸው ነው፡፡  

ግመል በፈሊጣዊ ንግግሮች ውስጥም ተደጋግሞ ይጠቀሳል፡፡ ከነርሱም ውስጥ “እንደ ግመል ሽንት ወደ ኋላ” የሚለው በጣም ታዋቂ ነው፡፡ ከተረትና ምሳሌዎች “ውሾቹ ይጮኻሉ፤ ግመሉ ግን ጉዞውን ይቀጥላል” የሚለው በጣም ዝነኛ ነው፡፡ “ግመሎች ያልፋሉ፤ ተራሮች ግን ለዘልዓለም ይኖራሉ” በሚል ርዕስ የሚጀምር የአርመን አጭር ልብወለድ በአማርኛ ተተርጉሞ በጣም ተወዳጅ ሆኖ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡

   ግመልን በመንተራሰስ የሚነገሩ ቂሳዎችን (ጥኡም ትረካዎችን) እንጥቀስ ካልን ደግሞ አንድ ገጽ ቀርቶ ሙሉ መጽሐፍ አይበቃንም፡፡ ለማሳረጊያ እንዲሆነን ግን ከዐረቢያ የተገኘውን ይህንን ውብ ትረካ ላጋራችሁ፡፡

*****

ሶስት ልጆች የነበሩት አንድ የዐረቢያ ሰው ነበር። ይህ ሰው በህይወቱ መጨረሻ አካባቢ ልጆቹን ጠርቶ እንዲህ አላቸው።
ልጆቼ ሆይ! በዚህ ምድር ላይ ስኖር የተገነዘብኩት ትልቁ ነገር የዕውቀት አስፈላጊነት ነው። ያለ ዕውቀት የሚሄድ ሰው በጭለማ እንደሚጓዝ በቅሎ ይደናበራል። ንግግሩም ሆነ ስራው አያምርለትም። ስለዚህ አዋቂና ታዋቂ እንድትሆኑልኝ እሻለሁ። ነገር ግን መምህራችሁን በጥንቃቄ መምረጥ አለባችሁ። ለዚህም ይረዳችሁ ዘንድ እነኝህን 17 ግመሎች ትቼላችኋለሁ። ታዲያ ግመሎቹን የምትከፋፈሉት በሚከተለው ቀመር መሰረት ይሁን።


የመጀመሪያው ልጄ የግመሎቹን 1/2 ይውሰድ።
ሁለተኛው ልጄ 1/3 ያህሉን ይውሰድ።
ሶስተኛው ልጄ 1/9 ያህሉን ይውሰድ።

ይህንን ስሌት በትክክል መፍታት የቻለውን ሰው እስከ መጨረሻው ድረስ መምህራችሁ አድርጋችሁ ያዙት።
አባታቸው ይህንን ተናዝዞ አረፈ። ልጆቹም አባታቸውን ከቀበሩ በኋላ ግመሎቻቸውን እየነዱ የተነገራቸውን ዓይነት መምህር መፈለግ ጀመሩ። በየከተማው ወዳሉ አዋቂዎች እየቀረቡአባታቸው በተሰጣቸው ስሌት መሰረት ግመሎቻቸውን እንዲያካፍሉአቸው ጠየቁ። ነገር ግን አንድም ሰው ስሌቱን መፍታት አልቻለም። ሌሎች በርካታ አዋቂዎችንም አማከሩ። ይሁንና ሒሳቡን አውቃለሁ የሚል ሰው ጠፋ።

በመጨረሻም አንደኛው ልጅለምን ጥያቄውንኸሊፋ ዓሊ ቢን አቡ ጣሊብ አናቀርበውም? ኸሊፋው ከቻሉ ስሌቱን ለራሳቸው ይፈቱታል። ካልቻሉም አንድ መላ ይመቱልናልየሚል ሀሳብ አቀረበ። ሌሎቹ ልጆችም በወንድማቸው ሃሳብ ተስማሙ። በዚሁ መሰረት ግመሎቻቸውን እየነዱ ወደ ዓሊ አቢ ጣሊብ (..) ዘንድ ሄዱና ጥያቄውን አቀረቡ። ዓሊ ኢብን አቡጣሊብ በነገሩ ትንሽ ካሰቡ በኋላ እንዲህ የሚል ምላሽ ሰጧቸው።


አስራ ሰባቱን ግመሎች በአባታችሁ ቀመር መሰረት ባከፋፍላችሁ ውጤቱ በክፍልፋይ (fraction) የሚገለጽ ይሆናል። እንደዚያ ከሆነ ግመሎቹን መቆራረጥ ሊኖርብኝ ነው ማለት ነው። ስለዚህ እንዲያ እንዳይሆን የራሴን አንድ ግመል ልጨምርበትና የግመሎቹ ብዛት 18 ይሁን። ይህ ከሆነ ዘንዳ የአባታችሁ ቀመር የሚቀጥለውን ውጤት ያስገኛል።

·        ታላቁ ልጅ ከጠቅላላው 1/2 ያግኝ በተባለው መሰረት ዘጠኝ ግመሎች ይደርሱታል::

·        ሁለተኛው ልጅ 1/3 ያግኝ በተባለው መሰረት ስድስት ግመሎች ይደርሱታል::

·         ሶስተኛው ልጅ 1/9 ያግኝ በተባለው መሰረት ሁለት ግመሎች ይደርሱታል።

·        ሶስታችሁ ያገኛችኋቸውን ግመሎች በአንድ ላይ ስንደምር (9+6+2) ውጤቱ አስራ ሰባት ይሆናል።

·        ከአስራ ስምንቱ አንድ ግመል ብቻ ይቀራል አይደል? እርሱ ደግሞ የራሴ በመሆኑ ወደኔ ይመለሳል።

ብልሁ ዓሊ ቢን አቢ ጣሊብ ሒሳቡን በዚህ አስገራሚ መንገድ ፈታው። ልጆቹምአባታችን የጠቆመን መምህር ይህ ነው በማለት እስከመጨረሻው ድረስ ተማሪዎቹ ሆነው ዘለቁ።
***** ***** *****
አፈንዲ ሙተቂ

ነሐሴ 24/2006

(አፈንዲ ሙተቂ)

የኢትኖግራፊ ፈረሳችን አንዳንዴ ከሰዎች ዓለም ይወጣል፤ ከዚህ ቀደም ወደ ጂንኒዎች ዓለም ሄደን ከዚያ ያገኘነውን ጨዋታ እያጫወትናችሁ በፍርሃት አርበድብደናችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ ፈረሳችን ወደ እንስሳት ዓለም በመሸጋገር እንደርሱ ጋላቢ ከሆነው ተአምረኛው “ግመል” ጋር ተፋጧል፡፡

        

ፈረሱም ፈረስ ነው፡ ግመሉም ግመል

ግመል ግን ይበልጣል በረሃ “እሚሸቅል”

እውነት ነው! ፈረስ በፍጥነቱ አንጀት አርስ ነው፡፡ በእሽቅድምድምና በግልቢያ አንደኛ ነው፡፡ በድሮ ዘመን ጦርነት ሲካሄድም ይህ ቀረሽ የማይባል አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ የሰው ልጅ እንስሳትን አላምዶ መጠቀም ከጀመረበት ዘመን አንስቶ ለሰዎች የሰጠው አገልግሎት ቢመዘን ግን ከግመል አይበልጥም፡፡ ለዚህም ብዙ ማስረጃዎች አሉን፡፡ አሁን እነርሱን አናስቆጥራችሁም፡፡ ጊዜው ሲደርስ ማስረጃዎቹ ራሳቸው እየጮኹ ይናገራሉ፡፡ Let the facts speak themselves እንዲሉ ፈረንጆች!!

ይልቅስ የዛሬው ጉዞአችን በረሀ ለበረሀ ስለሚያዟዙረን ግመልን ራሱኑ መጓጓዣችን ብናደርገውስ?… ይገባዋል! ለበረሃ ሐሩር፣ ለአሸዋ ውሽንፍር የማይበገረው “ግመሌ” ነው፡፡ ስለዚህ ፈረሳችንን በቆላው መሬት ውስጥ ለገበሬዎች በአደራ ሰጥተናቸው በግመል ጀርባ እየጋለብን ስለተአምረኛው እንስሳ እንዲህ እናወጋችኋለን፡፡

*****

የእንስሳው ስም “ግመል” ነው ብለናል፡፡ ይህንን ስም ልብ ብላችኋልን?….! እንግዲህ ተአምሩ የሚጀምረው ከዚህ ነው፡፡ “ግመል” የአማርኛው ስሙ ነው፡፡ በትግርኛም “ግመል” ነው፡፡ በእብራይስጥ ደግሞ “ጊመል” ነው፡፡ በግዕዝ “ገመል” ተብሎ ይጠራል፡፡ ዐረብኛው “ጀመል” ይለዋል፡፡ በሀረሪ ቋንቋ “ጋሚላ” እንለዋለን፡፡ እነዚህ ቋንቋዎች በሙሉ ሴማዊ ናቸው፡፡ እንስሳው በነዚህ ቋንቋዎች በተመሳሳይ/ተቀራራቢ ስም የሚጠራው ቋንቋዎቹ ስሙን በመወራረሳቸው አይደለም፡፡ ስያሜው የሴም ቋንቋዎች መነሻ ነው ተብሎ ከሚታመነበት ግንደ ሴማዊ ቋንቋ (Proto-Semitic Language) ተነስቶ በያንዳንዱ ቋንቋ ውስጥ እየተላለፈ ወደዚህ ዘመን ስለደረሰ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ እንስሳው ራሱ ከሰው ልጅ ጋር የተላመደው የሴም ህዝቦች መነሻ ከሆነው መካከለኛው ምስራቅ ውስጥ እንደሆነ ይጠቁመን ይሆን?..

በሚገባ! የሰው ልጅን የስልጣኔ ታሪክ ያጠኑ ምሁራን እንደሚመሰክሩት ግመልን ለመጀመሪያ ጊዜ ያላመዱት የሴማዊ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች ናቸው፡፡ በመሆኑም በአንዳንድ ቋንቋዎች (ኦሮምኛ፣ ሶማሊኛ ወዘተ…) እንስሳው የተለየ ስያሜ ቢኖረውም በዛሬው ዘመን አብዛኛው የዓለም ህዝብ ግመልን የሚጠራው ከሴማዊ ቋንቋዎች የወረሰውን ቃል በ“ማንሻፈፍ” (corrupt በማድረግ) ነው፡፡ ለምሳሌ እንግሊዛዊያን “ካሜል” ይሉታል፡፡ በጀርመንም “ካሜል” ይባላል፡፡ በፈረንሳይኛ፣ በስጳኝ፣ በጣሊያንኛና በሌሎችም የአውሮጳ ቋንቋዎች በተቀራራቢ ስም ይጠራል፡፡ እነዚህ ቋንቋዎች ቃሉን የወረሱት ከላቲን ነው፡፡ ላቲንም ከግሪክ ነው የወረሰው፡፡ ግሪክ ደግሞ በጥንቱ ዘመን በሶሪያና በፍልስጥኤም የብዙ ህዝቦች መግባቢያ ከነበረው የአረማይስጥ ቋንቋ ነው የወሰደው፡፡

ታዲያ ዛሬ ከምንጽፍባቸው ፊደላት መካከል አንዱ በዚህ እንስሳ ስም የተሰየመ መሆኑን የምታውቁት ስንቶቻችሁ ናችሁ?… በሮማዊያንም ሆነ በሳባ፣ በዐረብም ሆነ በግሪክ ፊደላት የምትጠቀሙት ሁሉ ከምትጽፉባቸው ፊደላት መካከል አንዱ በዚህ እንስሳ ስም የተሰየመ መሆኑን ተገንዘቡት፡፡ እንዴት ማለት “አሪፍ” ነገር ነው፡፡

“ሀረር ጌይ” በተሰኘው መጽሐፌ ለማስረዳት እንደሞከርኩት በዓለም ላይ ከሚሰራባቸው የፊደል ገበታዎች መካከል በጣም የሚበዙት ከአንድ ምንጭ ነው የተቀዱት፡፡ የሮማ ፊደል፣ የግሪክ ፊደል፣ የሳባ (ግዕዝ) ፊደል፣ የዐረቢያ ፊደል፣ የቄርሎሳዊያን (የሩሲያ) ፊደል እና የሳንስክሪት (ህንድ) ፊደል ምንጫቸው አንድ ነው፡፡ እርሱም የጥንቱ የፊንቃዊያን (Phoenicians) የፊደል ገበታ ነው፡፡ እነኚያ ፊንቃዊያን የመጻፊያ ፊደላትን ሲፈጥሩ እያንዳንዱን ፊደል በቅርብ በሚያውቋቸው ፍጥረታትና የሰው ልጅ የስራ ውጤቶች ነው የሰየሙት፡፡ ለምሳሌ “አሌፍ” ሲባል “በሬ” ማለት ነው፡፡ “ቤት” ደግሞ መጠለያችን የሆነው “ቤት” ነው፡፡ “ጊመል” ሲባል “ግመል” ነው፡፡ “ዳሌጥ” ደግሞ የቤት መግቢያ ምድራክ ነው፡፡ “ሚም” የሚፈስ ውሃ ማለት ነው፡፡ “ኑን” አሳ ማለት ነው፡፡  “ዐይን” ዐይን ነው፡፡ ወዘተ….

    

  የፊንቃዊያኑን ፊደል እንደ መነሻ በማድረግ የተፈጠሩት ልዩ ልዩ የፊደል ገበታዎች ሆሄያትን ያስቀመጡበት ቅደም ተከተል፣ የፊደላቱ ቅርጽና የመጠሪያ ስማቸው በዘመናት ሂደት ተለውጧል፡፡ ነገር ግን ወደ ኦሪጂናሌ አቀማመጣቸው ስንመልሳቸው ሁሉም ከአንድ ምንጭ የተነሱ መሆናቸውን በቀላሉ ማስተዋል ይቻላል፡፡ በዚህ መሰረት የዐረብኛ የፊደል ገበታ “አብጀድ” በተሰኘው ጥንታዊ አሰላለፉ ሲቀመጥ “ጂም” የሚባለው ሶስተኛ ፊደል በጥንቱ የፊንቂ ገበታ ላይ ከነበረው “ጊመል” የተገኘ መሆኑን ያዙልኝ፡፡ የኛው የሳባ ፊደል ገበታ በ“አቡጊዳ” ተራው ሲቀመጥ “ጊ” ከጥንቱ “ጊመል” የተገኘ መሆኑን እወቁልኝ፡፡ የእብራይስጡ “ጊመል”ም እንደዚያው፡፡ የግሪካዊያኑ “ጋማ”ም እንደዚያው፡፡ የእንግሊዝኛው (የ“ሮማ”ው) “ጂ”ም እንደዚያው…. ወዘተ….፡፡ እነዚህ ፊደላት ሁሉ አጠራራቸው ቢለያይም የፊንቃዊያኑን “ጊመል” መነሻ በማድረግ የተቀረጹ ናቸው፡፡ “ጊመል” ደግሞ የኛው “ግመል” ነው፡፡ ተአምረኛው እንስሳ!!  

*****

አላህ በቅዱስ ቁርኣን እንዲህ ይላል፡፡

 “ወደ ግመል አይመለከቱምን? እንዴት እንደተፈጠረች”

(አል-ጋሺያህ-17)

ቅዱስ ቁርኣን እንዲህ ያለው ነብዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ›ወ) እስልምናን ማስተማር ሲጀምሩ “ፈጣሪ የለም” ብለው በማስተባበል በተቃውሞ ለተነሱባቸው ሰዎች ነው፡፡ እነዚያ ሰዎች በንዳዱ ከታወቀው የዐረቢያ በረሃ ነው የተገኙት፡፡ በዚያ በረሃ ከምንም በላይ ዋጋ ያለው እንስሳ ግመል ነው፡፡ ግመሉ በአስቸጋሪው በረሃ እየኖረ በሚሰጠው አገልግሎት የሰዎች ኑሮ የተቃና እንዲሆን አድርጓል፡፡ እናም የቅዱስ ቁርኣን መልዕክት “እነዚያ ‘ፈጣሪን አናውቅም’ ባዮች የዚህን ድንቅዬ እንስሳ ባህሪ በማየት ብቻ የፈጣሪ መኖር በተከሰተላቸው ነበር” የሚል ነው፡፡

   እውነት ነው!! የበረሃው ሙቀት የቱንም ያህል ቢጨምር ግመሉ የመቋቋም ብቃት አለው፡፡ ግራር በቀል ከሆኑት የአዳማና የሀርዲም ቆላዎች አንስቶ እስከ ሰሜን አፍሪቃው የሰሐራ በረሃ እና የአፋር የዳሎል ስምጥ ቦታ ባሉት ሞቃት የዓለማችን ክልሎች ሁሉ የመኖር ብቃት አለው፡፡ ሌላው ቀርቶ ለርሱ የሚስማማ መኖ ካገኘ በደጋማ አካባቢዎችም (ውርጭ በሌለባቸው ማለቴ ነው) መኖር ይችላል፡፡

  በረሃው እንደ እሳት የሚፋጀው ቀን ቀን ነው፡፡ ሌሊት ላይ በተቃራኒው ብርዱ አይቻልም፡፡ ሙቀቱ በጣም ወርዶ “ደብረ ብርሃን ነው ያለሁት እንዴ?” ከሚያሰኝበት ደረጃ ይደርሳል፡፡ ሌሎች እንስሳት ለእንዲህ ዓይነቱ የአየር ለውጥ የተመቹ አይደሉም፡፡ ግመል ግን ሁሉንም ሳይቸገር ይቋቋማል፡፡

   ግመል ለምግቡም ቢሆን አይቸገርም፡፡ ዝናብ በተከታታይ ዓመታት ቢጠፋ እንኳ “መኖ ካላመጣህ” በማለት ባለቤቱን አያስጨንቀውም፡፡ ያገኘውን ዛፍና ቁጥቋጦ እየቀነጠበ ህይወቱን ማቆየት ይችልበታል፡፡ ለህይወቱ የሚያሰጋ በሽታም እምብዛም አያጋጥመውም፡፡ እርሱን የሚገድለው ወይ እርጅና ነው፣ ወይ የአንበሳ መንጋ ነው፡፡

 

   አዎን! ግመል የሚበላውንና የሚጠጣውን አጥቶ ሞተ ሲባል ታይቶም ተሰምቶም አይታወቅ!…! ግመል ከብትና ፍየል አይደለም፡፡ ምንም ነገር ሳይቀምስ ለብዙ ቀናት መቆየት ይችላል፡፡ ውሃ ሳይጠጣም ለሁለት ወር ያህል መቆየት ይችላል፡፡ ውሃ ከአካባቢው ጭራሹኑ ከጠፋ ባለቤቱን ራሱ እየመራው ውሃው ከሚገኝበት ስፍራ ይወስደዋል፡፡ ውሃውን ሲያገኝ ደግሞ አጠጣጡ ለጉድ ነው!! አንድ የፍየል መንጋ የሚያጠግበውን አሊያም አምስት በሬዎች የማይጨርሱትን ውሃ በአንድ ጊዜ ዥው አድርጎ መጠጣት ይችላል፡፡ ሆኖም ኢኮኖሚ የማያውቅ አይምሰላችሁ! ግመል እንዲህ የሚጠጣው በቂ ውሃ ባለበት አካባቢ ነው፡፡ ለምሳሌ የከረዩና የአፋር አርብቶ አደሮች ወደ አዋሽ ወንዝ እየመሩ ሲወስዱት ከወንዙ ውሃ እስኪበቃው ድረስ ይጎነጫል፡፡ ትንሽዬ የውሃ ጉድጓድ (ኤላ) ብቻ ባለበት ጭው ያለ በረሃ ግን ባለቤቶቹ በኦኮሌ እየጨለፉ የሰጡትን ብቻ ይጠጣና ያችኑ አብቃቅቶ ለወር ያህል ይቆያል፡፡

  የግመል ዋነኛው ተአምር “ሻኛው” ነው፡፡ እጅግ የደለበ የቅባት ስብስብ!! የሰውነቱ ስብና ሞራ በዚያ ላይ ነው የሚሰባሰበው፡፡ ምግብ ባጣ ጊዜ፣ አሊያም ውሃ በጠፋ ጊዜ በሻኛው ከተጠራቀመው ቅባት እየቆነጠረ እንደምግብ ይጠቀምበታል፡፡ ውሃውንም ከርሱ ያገኛል፡፡ አስቸጋሪ በሆነው የበረሃ ክልል ለመኖር የቻለውም ፈጣሪ “ሻኛ” የሚባለውን ድልብ ስለፈጠረለት ነው፡፡ ከሻኛው ጋር ሻኛውን እያቀለጠ የሚጠቀምበትንም ችሎታ ፈጥሮለታል፡፡ ታዲያ ይህ ችሎታ የተሰጠው ለርሱ ብቻ እንደሆነ ልብ በሉ!! ሻኛ ያላቸው ሌሎች እንስሳት በሙሉ ሻኛቸውን እያቀለጡ እንደ ምግብ ሊጠቀሙበት አይችሉም፡፡ ግመል ብቻ ነው ይህንን ማድረግ የሚችለው፡፡ የፈጣሪ ተአምር!!

(ይቀጥላል)

—-

አፈንዲ ሙተቂ

ነሐሴ 19/2006