የፊደል ጣጣና የአምስቱ ትውልድ ውዝግብ!
ሰሎሞን ተሰማ ጂ.
ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ “መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ” (1948) በታተመው መጽሐፋቸው ውስጥ እንደበየኑት፣ “ፊደል ማለት ቀለም፤ ምልክት፤ የድምፅና የቃል መልክ፤ ሥዕል፤ መግለጫ ማስታወቂያ፤” ነው (ገጽ 616)። ደስታ ተክለ ወልድም በበኩላቸው፣ በ1962 ዓ.ም. ባሳተሙት “ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት” መጽሐፋቸው እንደገለጹት፣ “ፊደል ማለት የነገር፣ የቃል ምልክት፣ የድምፅ ሥዕል፣ ማጉሊያ፤ መግለጫ ነው፤” (ገጽ 988)። በሁለቱም ሊቃውንት አተያይ ውስጥ ፊደል የድምፅና የቃል ምልክት መሆኑን በአጽንዖት ተገልጧል።