የቤት ልማቱ እና ሦስቱ ኢንቁፍቱ
ሰሎሞን ተሰማ ጂ.
በመጀመሪያ
በዘመነ ትምክህተኞችና ጠባቦች አንድ ቁስለኛ ሰው ነበረ። ይህ፣ በአድኃሪነት የተወጠረ የመሬትና የቤት ከበርቴ ድንገት ጋሬጣ ወግቶት ቅልጥሙ ቆሰለ። ያንንም ቁስል ንቆት ኖሮ፣ እያደር እያመረቀዘ ሄደና ደህና የዝንብ መሰብሰቢያ ቤት ወጣው። መጀመሪያ ላይ ንፍፊቱ፣ ቀጥሎ ግን መገረኑ ሰውዬውን አላስኬድ አላራምድ አለው። በየት በኩል ይላወስ። እግር ተወርች አሳሰረው። እቤቱ ዋለ። ዝንቡን እሽሽ ሲል ለመዋልም ተገደደ። የኋላ ኋላ ግን፣ ዝንቦቹን እሽሽ ማለቱንም ተወው።