የኛ ችግር፤ በተለይ የግንቦት ሰባት፤ “ከኤርትራ ሽሽት”

በየኔታ ተክሌ

ከዚያ ወደዚህ ስመለስ፤

ከአንድ ወር ቆይታ በሁዋላ ወደምኖርበት ከተማ ተመልሼ ከአውሮፕላን ዱብ ከማለቴ ነው ከአውሮፕላን ጣቢያ የተቀበለኝ ሰው “ፕሬዚዳንት ኢሳይያስ ሞቱ እየተባለ ይወራል” ብሎ ያረዳኝ። ይሄ ወዳጄ ዜናውን ሲሰብርልኝ፤ ስሜቴ ሁሉ ተሰባበረ። የኛ አገር ፖለቲካ ሁኔታ የባሰውን ጨለመብኝ። ሰማይ ተደፋብኝ። አዘንኩኝ። ደበረኝ። ለመሆኑ እኚህ 30 አመት ኢትዮጵያን የወጉና ምናልባትም የአገራችንን ያለፉትን 21 አመታት ታሪክ የቀያየረውን ሂደት የመሩ፤ አሁንም በብዙ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ እንደወዳጅ የማይታዩ ሰው ሞት ለምን አስደነገጠኝ? ብዙ ምስጢር የለውም። ባጭሩ የፕሬዚደንት ኢሳይያስ መሞት፤ የኤርትራን ፖለቲካ ሊለውጠው፤ ያ ደግሞ በተራው የኛን ያማራጭ ድርጅቶች (ተቃዋሚዎች የሚለውን ቃል አልወደውም) ጉዞ የባሰ ሊያዘበራርቀው ወይንም ሊያጨልመው ይችላልና የሚል ስጋት ነው።