የቃሊቲው ሚስጢር ገምጋሚ ሲገመገሙ (ከፋሲል የኔዓለም)
ወሰንሰገድ ገብረኪዳን “የቃሊቲው ሚስጢር” የሚል መጽሀፍ ማሳተሙን ተከትሎ አንድ ስማቸውን ያልገለጡ “የመጽሀፉ ገምጋሚ”በኢትዮሚዲያ እና በኢኤም ኤፍ ያቀረቡትን ጽሁፍ ተመለከትኩት። ፅሁፉ ከመውጣቱ በፊት ” እነ እከሌ እንዲህ አይነት ጽሁፍ ለማውጣት እየተሰናዱ ነው እና ነገሩን እንደ ስነልቦና ጦርነት አይተኸው፣ ንቀህ ተወው” የሚል ምክር አስቀድሞ ደርሶኝ ነበር ። እንደተባለውም ከሁለት ቀናት በሁዋላ ገምጋሚው የእኔን ስም ጎላ አድርገው በማቅረብ “የቃሊቲው ሚስጢር” የሚል ግምገማ ቢጤ ነገር ይዘውልን ብቅ አሉ። እውነቱን ለመናገር ለጸሀፊው መልስ የመስጠት ፍላጎት አልነበረኝም።
በግልጽ የሚታዩ ወይም በቀላሉ ሊረጋጋጡ የሚችሉ እውነታዎችን እንኳ ሳይቀር በመጠምዘዝ የሰዎችን ስብእና ለማጨቅየት የሚኳትኑ ሰዎች በሞሉባት አለም እንዲህ አይነት ነገሮች የተለመዱ ናቸው ። ጸሀፊውንም ከእነዚህ ሰዎች መካከል እንደ አንዱ አድርጌ ቆጥሬያቸዋለሁ። ባላደርገው ደስ ባለኝ ፣ ግን አልቻልኩም። አንድ ጓደኛየ “ምናልባት ብልሹ የመጽሀፍ አገማገም ባህሪያት”ን ለማወቅ ይጠቅመን ይሆናልና የሚሰማህን ብትናገር ጥሩ ነው ብሎ ስለገፋፋኝ ነው ትንሽ ለመተንፈስ የፈለኩት። በህይወቴ ውስጤ ደስ ሳይለኝ ከጻፍኩዋቸው ጽሁፎች መካከል አንዱ ይህ ነው፣ ጽሁፌ “ራስን መከላከል” ወይም “እኔ”ን ማሳያ ተደርጎ በአንባቢዎች ዘንድ ሊታይ ይችላል በሚል ርደት ላይ ነኝ። በእውነት ስለራሳቸው የሚጽፉና የሚናገሩ ሰዎች እንዴት ታድለዋል!
ስም አልባው ገምጋሚ ጽሁፋቸውን ሲጽፉ የሊጆክ መምህራን fallacy of ignorance ( appeal to ignorance) የሚሉትን ግምት ውስጥ ያስገቡ ይመስላል። “አንባቢዎች የጽሁፌን እውነትነት ለማረጋገጥ ስለማይችሉ፣ የጻፍኩትን እውነት ነው ብለው ይቀበሉታል ፣ ስለዚህም የፋሲልን (ከቻልኩም) የደረጀ ሀብተወልድን ማንነት ለማፈራረስ ከዚህ በላይ ጥሩ አጋጣሚ የለምና ልጠቀምበት” ያሉ ይመስላል ። ወደ ዝርዝሩ ሳልገባ በቅድሚያ…
(በቅድሚያ ) የቃሊቲ ባልደረባየ የነበረው ወሰን ሰገድ ገብረኪዳን መጽሀፍ በማሳተሙ በእጅጉ ተደስቻለሁ። ወሰን ብዙ ተሰቃይቷል። አብዛኛውን ጊዜ እሱ ባልጻፋቸው ጽሁፎች ( በዋና አዘጋጅነት ስሙ ስለተቀመጠ) ፍርድ ቤት ተመላልሷል። ወሰንን በስራ አለም ብዙ አላውቀውም። አዲስ ዜና ውስጥ ከሁለት ወር በላይ የሰራ አይመስለኝም። ያኔም ቢሆን ከአራት ቀናት ለበለጠ ጊዜ በአንድ ቢሮ ውስጥ ተገናኝተን አብረን ለመስራታችን እጠራጠራለሁ፤ ብዙውን ጊዜ የሚያገናኘን ደሞዝ ወይም የደሞዝ አጋማሽ ክፍያ ነው። ወሰን የስነጽሁፍ ዝንባሌ እንዳለው ያወኩት እስር ቤት ነው። በእስር ቤት ውስጥ አንድ ጊዜ ለእጮኛየ ሌላ ጊዜ ደግሞ ለፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም የልደት ቀናት ውብ ግጥሞችን ገጥሞልናል ። አብረን የሰራንባቸው ጊዜዎች አጭር መሆን፣ በእነዚህም ጊዜዎች ቢሆን አዘውትሮ ቢሮ የማይገኝ በመሆኑ እንዲሁም እሱን እንድንቀጥረው ያግባባን ሰው የሰጠን መረጃ የተሳሳተ መሆን የወሰንን የስነጽሁፍ ችሎታ ሳንጠቀምበት ቀርተናል። ብዙ ጋዜጠኞቻችንን የሚያዘናጋብን የ”ጀበና ቤት” ቋሚ አባል በመሆኑም እንዳላውቀው አድርጎኛል።። ወሰን ራሱም በመጽሀፉ እንደገለጠው ” በጣም ግራ የሚያጋባ” (odd) የሚባል ሰው አይነት በመሆኑና ስራ በጀመረ ማግስት ከሌሎች ባልደረቦቹ ጋር የፈጠረው ውዝግብ ወሰንን እንዳላውቀው ተጫማሪ ምክንያት ሳይሆን አይቀርም። በተቀጠረ በሳምንቱ ነው አቤቱታ መስማት የጀመርኩት። በእስር ቤት ግን ወሰንን በደንብ ለማወቅ ችያለሁ። ጥቃትን የማይወድ ደፋር በመሆኑ እወደዋለሁ። አዛኝ እና ለምንም ነገር የማይጨነቅ ነው። የመግጠም ችሎታው ልዩ ነው። በመጽሀፉ ውስጥ ስለራሱ የእስር ቤት ቆይታ የገለጠበት መንገድ በሌሎች ታሳሪዎች ዘንድ ትዝብት ላይ እንዳይጥለው ግን እሰጋለሁ ። የኢህአዴግ ባለስልጣናት ከቅንጅት መሪዎች የተሻለ ስነምግባር እንደተላበሱ አድርጎ ያቀረበበት ክፍል፣ “ወሰን የትግል ታሪኩን “ለጀበና” ሲል ለውጦት ይሆን?” የሚል ጥያቄ አሳድሮብኛል። ሰዎች ለመኖር ሲሉ እምነታቸውን ይሸጣሉ፣ ወሰን ግን እንዲህ በቀላሉ የሚሸጥ ሰው አለመሆኑን እመሰክራለሁ። በርግጥ በእኔ ላይ የሚያቀርበው ተደጋጋሚ ወቀሳ ” በገንዘብ አልደገፈኝም” የሚል በመሆኑና እኔም የነበርኩበት እና ያለሁበት ሁኔታ ያንን ለማድረግ ስላላስቻለኝ ለወሰን ስሜት መጎዳት አስተዋጽኦ አድርጌ ይሆናል። የወሰን ጽሁፍ የአዲስ ዘመንን ሽፋን አገኘ ሲሉኝና የአሳታሚዎችን ማንነት ሲነግሩኝ፣ ወሰን ባላወቀው ወይም ሆን ብሎ ለመኖር ሲል ፈቅዶ የአሳዳጆቹ መጠቀሚያ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ። ያም ሆነ ይህ ግን ወሰን ሊደገፍና ሊበረታታ የሚገባው ብዙ መስዋትነትን የከፈለ ጋዜጠኛ ነው። መጽሀፉ እንዲሸጥለትም እመኝለታለሁ።
ወሰን እኔን በተመለከተ የተወሰኑ ጥሬ ሀቆችንና አስተያየቶችን አስፍሯል። ጥሬ ሀቆችን በተመለከተ አንድ ቀን አእምሮው ሰከን ሲል ወይም በነጻነት የመጻፍ እድሉን ሲያገኝ እንደሚያስተካክላቸው አምናለሁ። ጊዜ አይሽሬ መጽሀፍ ለመጻፍ ስነምግባርን እስከ አፍንጫ መታጠቅ ግድ ይላል፤ ወሰንም አንድ ቀን ያንን ከኒውክሊየር የበለጠ ሀይል ያለውን የስነምግባር ትጥቅ ይታጠቀዋል ብየ አምናለሁ። ስነምግባር ከነጻነት ጋር የተያያዘ ነው። እንደ ማንዴላ ያሉት ሰዎች “ልዩ ፍጠረት” የተባሉት ነጻነት በሌለበት ሁኔታ የስነምግባር የበላይነት በማሳየታቸው ነው። ነጻነት ባለበት አገር አብዛኛው ሰው ወዶም ይሁን ሳይወድ የስነምግባር ትጥቅ ይታጠቃል። ያንን ቀን እናፍቃለሁ።
ወሰን በእኔ ላይ ያቀረባቸውን አስተያየቶች በተመለከተ ግን የጸሀፊው የግል እይታ ውጤቶች በመሆናቸው አልከራከርም። አስተያየየት ከጥሬ ሀቅ የሚለየው ግላዊ ( subjective) በመሆኑ ነው። አስተያየት በግል አለመግባባት ወይም በሌሎች ተገቢ ወይም ተገቢ ባልሆኑ ነገሮች ላይ ተመስርቶ ሊሰጥ ይችላል። ለአንዱ ቅዱስ የሆነ ሰው ለሌላው እርኩስ ሊሆን ይችላል። ሰይጣን ከእግዚአብሄር ይሻላል ብለው የሚከራከሩትን ሰዎች ተሳስታችሁዋል ልንላቸው አንችልም፤ እይታቸው ነውና። ወሰን በእኔ ላይ ስለሰጠው አስተያየትም ምንም አይነት ቅሬታ የለኝም፤ እንዴውም “አንደኛው ማንነቴ እንዲህ ነው እንዴ ? ሰዎች በዚህ መንገድ ይመለከቱኛል እንዴ?” እያልኩ ራሴን እንድጠይቅና እንድገረም አድርጎኛል። በዚህም አመሰግነዋለሁ ። ወደ ተነሳሁበት ልመለስ።
የቃሊቲ ሚስጥሮችን ገመገምኩ በማለት ስለ እኔ የጻፉት ሰው ወሰን ስለ እኔ ከጻፈውም በላይ ብዙ እርምጃ ተጉዘው ጽፈዋል። “ገምጋሚው” ስማቸውን አለመጥቀሳቸው በሚገመግሙት መጽሀፍ ላይ እምነቱ የላቸውም ብለን ልንገምት እንችላለን፣ ነገር ግን መጽሀፉን እንድናነበው ምክረውናልና ግምቱ አይሰራም። ገምጋሚው መንግስትን ፈርተው ነው ስማቸውን ያልገለጡት ብለን ልንገምትም እንችላለን። ጽሁፋቸውን ካየን ግን “አሸባሪን ያጋለጡ ጀግና “ተብለው ይወደሳሉ እንጅ አያስከስሳቸውም። ምናልባት ገምጋሚው በራሳቸው የማይተማመኑ ሰው ሊሆኑ ይችላሉ።
ገምጋሚው ወሰን በመጽሀፉ “በስም እየጠቀሰ የሚተቸው የስራ ባልደረባውን ፋሲል የኔአለምን ብቻ ነው” ሲሉ ጽፈዋል። ይህ ነጭ ውሸት ነው። ወሰን ያልተቸው ጋዜጠኛ የለም፣ አንዳንዶችን በፍርሀት ሌሎችን በአስመሳይነት (ታፔላነት)፣ አሳታሚዎችን ደግሞ የሌሎችን ስራ የራሳቸው አድርገው በማቅረብ። (ወሰን እነ ወናግሰገድ ዘለቀን፣ አንዱለአም አየለንና ናርዶስ መአዛን በፈሪነት ለመተቸት መሞከሩ አሳዝኖኛል፤ እነዚህ ሰዎች በእነ እስክንድር ነጋ ላይ መስክራችሁ ከእስር ቤት ውጡ ሲባሉ አናደርገውም ብለው በጽናት የቆሙ ናቸው። አንዱአለም ሩህሩህና እጅግ ሰው ወዳድ በመሆኑ እኛ አስቀድመን በመፈታታችንና ከእኛ በመለየቱ አዝኖ ቢያለቅስ አይገርምም፤ ባያለቅስ ነበር የአንዱአለም የሰው ፍቅር የይምሰለን ነው ብለን ልንተቸው የሚገባ።)
ገምጋሚ ይቀጥሉና ወሰን “ፋሲል የኔአለም የማወቅና የመታወቅ በሽታ ያለበት እንደሆነ ገልጾታል” ይላሉ። ወሰን ስለ እኔ የገለጠው እንዲህ ይላል ” እርግጥ ነው ፋሲል የኔአለም ከራሱ የሚተርፍ በቂ እውቀት አለው። አንባቢ ነው። የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የዲግሪ ምሩቅ ነው። በትምህርት ደረጃ እስር ቤት ከምንገኘው ጋዜጠኞች ሁሉ ከፍተኛውን ቦታ የሚይዝ ነው። ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ የሚያደርገውን ነገር በደንብ ያስተዋለ ሰው ‘ ይሄ ልጅ የአዋቂነትና የታዋቂነት በሽታ አለበት እንዴ‘ ብሎ እንዲጠይቅ መገደዱ አይቀርም።” ልብ በሉ አንባብያን! ወሰን ጥያቄ ነው ያቀረበው፣ የማወቅና የመታወቅ በሽታ እንዳለብኝም እርግጠኛ መሆን አልቻለም፤ ገምጋሚው ግን “ወሰን ፋሲልን የማወቅና የመታወቅ በሽታ አለበት ይለዋል” ይሉናል። ወሰን እዚህ መደምደሚያ ላይ ለምን እንደደረሰ ሲናገር እንዲህ ይላል፡ ” ሁላችንም የዶ/ር ያእቆብን አንባቢነት እናደንቃለን። የእሱ ግን ይለያል። ያነበበውን መጽሀፍ ሀሉ ለማንበብ የሚያደርገው ጥረት ይገርማል።” ገምጋሚው ይህን ሁሉ መነሻ ሳይዳስሱ ነው አንባቢያንን ሊያሳስቱ የሞከሩት ።
ገምጋሚው አሁንም ይቀጥሉና” እስር ቤት እያሉ ፋሲል የኔአለም ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሰጠው ቃል በታሳሪዎች እጅግ እንደተጠላ” ጽፏል ይላሉ። ወሰን የሚለው በእስር ቤት ውስጥ ስንገባ ፋሲል በኢቲቪ በሰጠው ቃል በተናገረው ብዙ ሰዎችን እንዳስከፋ ያወኩት ከ2 ወራት በሁዋላ ነው…አንድ አምስት ያክል እስረኞች እንደተናደዱበት ነገረውኛል ” ነው። ገምጋሚው “ፋሲል በእስረኞች በእጅጉ የተጠላ ነበር የሚለውን” ከየት ነው ያገኙት? ምናልባት ለወደፊቱ ከሚወጣ የወሰን መጽሀፍ አግኝተውት ይሆን? ( ለማስታወሻ፦ ይህ ጥሬ ሀቅን የተመለከተ በመሆኑ፣ ወሰን አንድ ቀን በጋዜጠኞች እንዴት እንደተመረጥኩ፣ ምን እንድናገር እንደተወከልኩ፣ ኢቲቪ የትኛውን ንግግሬን ቆርጦ የትኛውን እንዳስተላለፈው ለወደፊቱ ነጻነቱ ሲገኝ ኢቲቪ የመረጃ ክፍል በመሄድ ሀቁን እንደሚያወጣው ተስፋ አደርጋለሁ። በእስር ቤት ውስጥ የተጠላሁ ሰው ከነበርኩ ግን ዛሬ አብረውኝ የሚሰሩ በርካታ የቃሊቲ ባልደረቦቼ እስከዛሬ ስላልነገሩኝ በእውነት አዝንባቸዋለሁ። አንድ ስሙን የማልጠቀሰው የእስር ቤት ባልደረባየ ከኢትዮጵያ ደውሎ ” ፋሲል ወሰን ላንተም እኮ አልተመለሰም” ብሎኛል)።
ገምጋሚው ከወሰን መጽሀፍ ለቃቅመው ስለ እኔ ያቀረቡዋቸው አሉታዊ ትችቶች እነዚህ ናቸው። ሁለት ምክሮችን ብቻ ለገምጋሚው ላቅርብና ልሰናበት። ምክር አንድ ፦ አገር የሚያድገው እርስ በርስ በመጠፋፋት ሳይሆን እጅ ለጅ በመያያዝ ነው። በዚህ አለም የምንኖረው ለአጭር ጊዜ ነው። በዚህ አጭር ጊዜ ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ስራ ስርተን ማለፍ ይገባናል። አንዱ አንዱን ቢያጠፋ ትረፉ መጠፋፋት ነው። ምክር ሁለት ፦ አንድ መሪ ማንነቱን በጭብጨባ ወይም በውዳሴ ላይ የሚገነባ ከሆነ፣ ጭብጨባው እና ውዳሴው በቆመ ጊዜ መሪው ይፋራርሳል። እንዲህ አይነት ጽሁፎች ሰዎችን ለማፈራረስ የሚችሉት ማንነታቸውን በጭብጨባና በከንቱ ውዳሴ የገነቡትን ብቻ ነው። ብዙ ሰዎች ሲፈራርሱ ያየነውም ለዚህ ነው።
የመጨረሻው መጨረሻ – ወሰን ካስታወሰኝ ትዝታዎች ውስጥ ይህችን ልመርቃችሁ ፡” በብርበራው መጨረሻ ላይ በቢሮአችን በሰነድነት የተያዙ ፎቶዎች በሙሉ ይታዩ ጀመር። መርማሪዎቻችን አንድ ፎቶ ያነሱና “ይሄ የማን ነው?” ይሉናል።
“ዶ/ር እከሌ”
“ይሄስ?”
አርቲስት እከሌ
እንዲህ እንዲህ እያሉ በርካታ ፎቶዎችን ያዙ። አብዛኞቹ ፎቶዎች ከእኛ ጋር አብረውን የታሰሩ የቅንጅት አመራሮች ነው። እኔና ፋሲል የፎቶ ምርጫቸው ስለገረመን ሆን ብለን የልደቱ አያሌውን ፎቶ እያወጣን “ይህንንስ አትፈልጉትም”ማለት ቀጠልን። መርማሪዎች የልደቱን ፎቶ ይቀበሉንና ፈገግ እያሉ በአስረጅነት ወደ ማይፈልጉዋቸው ፎቶዎች ጋር ይቀላቅሉታል። ይህ ሁኔታ በእኛ ልብ ውስጥ ገረሜታን እንዳጫረ ከምሽት 1 ሰአት ሊሆን 20 ደቂቃ ሲቀር ብርበራው አለቀና ወደ ማረፊያችን ተመለስን።