በዓሉ የማን ነው ?
ኢየሩሳሌም ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ምኒሊክ እኤአ በ1928 ዓም ባሠሩት ሕንፃ ውስጥ ሆኜ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የሚያስተላልፈውን የዓመት በዓል መርሐ ግብር እየተመለከትኩ ነበር፡፡
መርሐ ግብሩ በሚደረግበት አዳራሽ መድረክ ላይ ለበዓሉ የመልካም ምኞት መግለጫ ተጽፏል፡፡ «ለክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን ለፋሲካ በዓል አደረሳችሁ» ይላል፡፡ ይህ ነገር በሞባይል የድርጅቶች መልእክቶች እና በመልካም ምኞት መግለጫ ካርዶችም እየተለመደ ነው፡፡
ለምን? አልኩ፡፡ ምናለ «እንኳን ለፋሲካ በዓል አደረሳችሁ» ቢባል ምናለበት፡፡ ለምንድን ነው ሌላኛው ወገን አይመለከትህም የሚባለው? እኔ ራሴ ነኝ የፋሲካም ሆነ የመውሊድ በዓል አይመለከተኝም ማለት ያለብኝ እንጂ ጋዜጠኛው ወይንም ባለ ሥልጣኑ፣ ወይንም ደግሞ ባለ ካርዱ ለምን አይመለከትህም ይለኛል? በመኖር እና በመስተጋብር ብዛት እሴቱን ገዝቼው የኖርኩትን በዓል ለምንስ ይነጥቀኛል?
መጀመርያ ነገር የፋሲካ በዓል የክርስትና እምነት በዓል ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱም ብሔራዊ በዓል ሆኖ ታውጇል፡፡ በዚህ ቀን እንዲያርፉ የተፈቀደው ክርስትናን ለሚያምኑ ብቻ አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ሁሉም ነዋሪዎች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል በዚህች ሀገር ውስጥ አንደኛው የሌላኛውን በዓል ሲያከብሩ ነው የኖሩት፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በዓልን በሁለት ዓይነት መንገድ ነው የምናከብረው፡፡ አንደኛው የበዓሉን ትርጉም እና ዓላማ በመቀበል ሲሆን ሌላኛው ደግሞ የበዓሉን ባለቤቶች በማክበር ነው፡፡
የበዓሉን ዓላማ እና ትርጉም በመቀበል የሚያከብሩት ያን በዓል የተደረገበትን ምክንያት የሚያምኑ፣ ከበዓሉ በረከት እናገኛለን ወይንም መንፈሳዊ ጥቅም እናገኛለን ብለው የሚያስቡ፣ በዓሉ በሕይወታችን ውስጥ ትርጉም አለው ብለው የሚያስቡ ናቸው፡፡ ለምሳሌ የመውሊድን በዓል ሙስሊም ወገኖቻችን ሲያከብሩት፣ የትንሣኤንም በዓል ክርስቲያን ወገኖቻችን ሲያከብሩት በዚህ እሳቤ ነው፡፡
ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የበዓሉን ባለቤቶች በማክበር ነው፡፡ ምንም እንኳን በበዓሉ ሃይማኖታዊ፣ፖለቲካዊ ወይንም ማኅበራዊ ትርጉም እና እሴት ባይስማሙም፣ የበዓሉ ባለቤቶች ግን ወገኖቻቸው በመሆናቸው የተነሣ በዓላቸውን በዓላቸው ያደርጉታል፡፡ የሰውን ደስታ መካፈል የላቀ ማኅበራዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ደረጃ ነው፡፡ ሰው በኅሊና ምጥቀት እያደገ ሲሄድ የሚደሰተው ለራሱ በሚያገኘው ነገር ሳይሆን ሌሎች በሚያገኙት ነገር ነው፡፡ በሌላ ሰው ልብስ ላይ የሚረጭ ሽቱ ያልተረጨውንም እንደ ሚያረካው ሁሉ፣ ሌላው ሰው የሚያገኘው ደስታም ከመነሻ የደስታው ባለቤት ያልሆነውንም ሰው በመካፈል ስሌት ያስደስተዋል፡፡
በዚህም የተነሣ መውሊድ ኢትዮጵያ ውስጥ የሙስሊሞች ብቻ በዓል አይደለም፡፡ የኢትዮጵያውያን በዓል ነው፡፡ የሙስሊሞች ደስታ የክርስቲያኖችም ነውና፡፡ የሙስሊሞች ወደዚያ በዓል መድረስ የክርስቲያኖችም መድረስ ነው፡፡ መውሊድን እንደ በዓል የሚቆጥር ሁሉ ሙስሊሞች ለበዓሉ በሚሰጡት ሃይማኖታዊ ትርጓሜ የመስማማት ግዴታ የለበትም፡፡ ያ በዓል ለወገኖቹ በሚሰጠው እርካታ እና እሴት መስማማት እንጂ፡፡ የፋሲካም በዓል እንዲሁ ነው፡፡ በሕግም ሆነ በማኅበራዊ ተራክቦ የተነሣ በዓሉ የኢትዮጵያውያን በዓል ሆኗል፡፡ ለዚህ ነው በፋሲካ በዓል ሙስሊሞች ከክርስቲያኖች ጋር ሲገናኙ «እንኳን አደረሳችሁ» እንጂ እንኳን ለበዓላችሁ አደረሳችሁ የማይባባሉት፡፡ በመውሊድ ጊዜም ቢሆን «እንኳን አደረሳችሁ» ይባባላሉ እንጂ «እንኳን ለሙስሊሞች መውሊድ አደረሳችሁ» የማይባባሉት፡፡
ለምሳሌ በእስራኤል ሀገር ትንሣኤም ሆነ መውሊድ ብሔራዊ በዓላት አይደሉም፡፡ ሚዲያዎቻቸውም «እንኳን ለክርስቲያኖች ትንሣኤ አደረሳችሁ» ወይንም «ለሙስሊሞች መውሊድ አደረሳችሁ» ቢሉ አይገርመኝም፡፡ ሲጀመር ሀገሪቱም ብሔራዊ በዓል አላደረገችውም፣ ሲቀጠልም አንዱ የሌላውን በዓል በመከባበር እሴት ተቀብሎ አልኖረም፡፡
ኢትዮጵያ ግን የተለየች ናት፡፡ እነዚህ ሃይማኖታዊ በዓላት የሀገሪቱ ጉዞ አካል ሆነው፤ የሀገሪቱን አሴቶች ቀርጸዋል፡፡ ወደድንም ጠላንም በእነዚህ እሴቶች ተጽዕኖ ውስጥ አልፈናል፡፡ በበዓላቱ ምክንያት እህልም ተወደደ፣የበግ ዋጋም ጨመረ፣ ዕንቁላልም አራት ብር ገባ፣ ዶሮም በመቶ ሃምሳ ብር ተሸጠ ዋጋው እምነትን ለይቶ አያስከፍልም፡፡
እንዲያውም ሚዲያዎቹ ከበረቱ አንድ ማስለመድ ያለባቸው በጎ ባህል አለ፡፡ ይህንን ግብጾች ይፈጽሙታል፡፡ «በክርስቲያኖች» በዓል ላይ የሙስሊም መሪዎች፣ «በሙስሊሞቹም» በዓል ላይ የክርስትና እምነት አባቶች «እንኳን አደረሳችሁ» እንዲሉ ማበረታታት ያስፈልጋል፡፡ አንድን ወገን እንኳን አደረሰህ የምንለው ያ ወገን ከሚያስበው ዋጋ አንፃር እንጂ ያንን ዋጋ በእኛ መመዘኛ መዝነን መሆን የለበትም፡፡ ወይንም የእነርሱን ያህል በበዐሉ ጠቅላላ ጉዳዮች ተስማምተን መሆን አይገባውም፡፡
ያለበለዚያማ የግንቦት ሃያ በዓል «ለኢሕአዴግ አባላት እና ደጋፊዎች በሙሉ እንኳን ለግንቦት ሃያ በዓል አደረሳችሁ» ተብሎ ሊጻፍ ነው ማለት ነው፡፡ በበዓሉ እሴቶች፣ በበዓሉ ቀን፣ በበዓሉ ምክንያት፣ በበዓሉ ትርጉምም የማይስማሙ ወገኖች አሉ፡፡ የሀገሪቱን በዓላት የማወጅ ሥልጣን የተሰጠው አካል እስካወጀ ድረስ ግን በዓሉ የኢትዮጵያ በዓል ሆኗል፡፡ ልክ መስከረም ሁለት የሀገሪቱ በዓል እንደነበረው ማለት ነው፡፡
እና እባካችሁ ቀላል በሚመስሉ፣ ነገር ግን አላስፈላጊ ልዩነትን በሚለጥጡ፣ የማኅበረሰባችንን የአንድነት እና የመስተጋብር እሴት በሚያፈርሱ ነገሮች ላይ መትጋታችንን ብናቆም ምናለ፡፡ በተለይ ጋዜጠኞች እና በሞባይል ስልክ መልእክት የምትልኩ ድርጅቶች፡፡