ሰብአ ሰገል
(click here for pdf) በየዓመቱ የልደት በዓል በመጣ ቁጥር ከሚነሡ ሰዎች መካከል ናቸው፡ ሰብአ ሰገል፡፡ ማናቸው? ከየት መጡ? ሀገራቸው የት ነው? ስንት ናቸው? ለምን ዕጣን፣ ከርቤ እና ወርቅ አመጡ? የሚሉት ጉዳዮችም አብረው ይነሣሉ፡፡
ስለ ሰብአ ሰገል የመጀመርያውን መረጃ የሰጠን ቅዱስ ማቴዎስ ነው፡፡ ማቴዎስ በወንጌሉ በምእራፍ ሁለት ላይ የጥበብ ሰዎች መሆናቸውን፣ የመጡት ከምሥራቅ መሆኑን፣ የተመሩት በኮከብ መሆኑን፣ የመጡበት ዘመን ንጉሥ ሄሮድስ ይሁዳን ሲገዛ መሆኑን፣ ሕፃኑ በተወለደ ጊዜ መድረሳቸውን፣ ዕጣን፣ ከርቤ እና ወርቅ በእጅ መንሻነት መስጠታቸውን፣ በኋላም ደስ ብሏቸው በሌላ መንገድ ወደመጡበት መመለሳቸውን ይነግረናል፡፡
መጀመርያ የሚነሣው ጥያቄ እነዚህ «ሰብአ ሰገል» እነማን ናቸው? የሚለው ነው፡፡ «ሰብአ ሰገል» ማለት በግእዙ «የጥበብ ሰዎች» ማለት ነው፡፡ በየሚዲያው ታላላቅ የሚባሉት የሥነ ጽሑፍ ሰዎች ሳይቀሩ ሰብአ ሰገል የሚለውን «ሰባዎቹ ሰገሎች» እያሉ የገለጡልንን በአፈ መላእክት ያርምልን ብለን ወደቀጣዩ እንሻገራለን፡፡
እነዚህን ሰዎች በእንግሊዝኛው ሐዲስ ኪዳን magi ይላቸዋል፡፡ ይህም magus የሚለው የላቲኑ ቃል ብዙ ቁጥር ነው፡፡ የላቲኑ ቃልም magos ከሚለው የግሪኩ ቃል የመጣ ሲሆን እርሱም ቢሆን maguŜ ከሚለው የጥንት ፋርሶች ቋንቋ አቨስታን የተገኘ ነው የሚሉ አሉ፡፡ በፋርስ magâunô የተሰኘው ሃይማኖታዊ ማኅበረሰብ በኋላ ዘመን ዞራስተረስ የተገኘበት ነው፡፡
በዚህ ማኅበረሰብ ዘንድ ካህናቱ ከፍ ያለ ቦታ ያላቸው ሲሆን የከዋክብትን ነገር መከታተልም ዋነኛው ተግባራቸው ነበር፡፡ እንዲያውም አንዳንድ መዛግብት በሀገራችን የሚገኘው ዐውደ ነገሥት ከእነዚህ አካላት የተቀዳ የከዋክብት ጥናት ነበረ ይላል፡፡ በኋላ ዘመን ግን ከጥናትነት ወደ ጥንቆላ መሣርያነት ወረደ፡፡
ሥነ ከዋክብትን ለጥንቆላ ማዋል በብዙ ማኅበረሰቦች ዘንድ የተለመደ ነገር ነው፡፡ የሥነ ከዋክብት ተመራማሪዎቹ ከፍ ያለ ዕውቀት እንዳላቸው ስለሚገመት ይህንን ዕውቀት የያዙ አንዳንዶች በከዋክብት ምሕዋር ተጠቅመው የወደፊቱን እንደሚተነብዩ መናገር ጀመሩ፡፡ በዚህም የተነሣ ሥነ ከዋክብት እና ጥንቆላ የተዛመዱ ሆኑ፡፡ የእንግሊዘኛው ቃል magic የተገኘውም ከዚሁ አስተሳሰብ ነው ይባላል፡፡ በኛም ሀገር «ኮከብ ቆጣሪ» ማለት «ጠንቋይ» እንደ ማለት ሆኗል፡፡
አንዳንድ ሊቃውንት ነቢዩ ዳንኤል የንጉሡን ሕልም በመተርጎሙ የተነሣ ናቡከደነፆር «ለባቢሎን ጠቢባን ሁሉ አለቃ» እንዳደረገው የተገለጠውን በመያዝ በማቴዎስ ወንጌል ሰብአ ሰገል የተባሉት ከዚህ የፋርስ ምድር የመጡት ጠቢባን ናቸው ይላሉ፡፡ የዚህንም ምክንያት ሲያስረዱ ዳንኤል ሕልሙን ሲተረጉም የተሰጠው መዓርግ Rab-mag የሚል ነው፡፡ ትርጉሙም «ሊቀ ጠቢባን» እንደ ማለት ነው፡፡ ማቴዎስም ሰብአ ሰገልን ሲገልጣቸው በዚሁ ቃል ነው የተጠቀመው የሚል ነው፡፡
ማቴዎስ ሀገራቸውን «ከምሥራቅ» ብሎ መግለጡ የመጡት ከባቢሎን ወይንም ከፋርስ መሆኑን ለመንገር ነው ብለው የሚተረጉሙም አሉ፡፡ ፋርስ ለእሥራኤል ምሥራቅ ነውና፡፡
አንዳንድ መዛግብት ደግሞ በፋርስ አካባቢ የሚኖሩ የአዳም ልጅ የሴት ዘሮች ነበሩ ይላሉ፡፡ እነዚህ ዘሮች ከሴት የወረሱት አንድ የብራና ጥቅልል ነበራቸው፡፡ በዚህ ጥቅልል ላይም «ወደፊት ንጉሥ በይሁዳ ይወለዳል፡፡ ኮከብ በምሥራቅ ስታዩ ሄዳችሁ ስገዱለት» የሚል ጽሑፍ ነበረው፡፡ አባታቸውም ለንጉሡ የሚሰጥ ስጦታ ሰጥቷቸው ነበር ይላሉ፡፡ እነዚህም ሰዎች ጌታ ሊወለድ ጥቂት ጊዜ ሲቀረው ያንን ኮከብ አዩ፡፡ ወዲያውም እየተከተሉት ቤተ ልሔም ደረሱ፡፡
ይህ ገለጣ በኢትዮጵያ ትውፊት ከሚነገረው ጋር በመጠኑ ተመሳሳይ ነው፡፡ ሰብአ ሰገልን የሴት ልጆች ማድረግ በኢትዮጵያ ጥንታውያን መጻሕፍትም እናገኘዋለን፡፡ ለጌታ የተሰጡት ሦስቱ ስጦታዎች ከአዳም ሲያያዙ መጥተው በሴት በኩል ለልጅ ልጆቹ መድረሳቸውን የማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜ ይነግረናል፡፡
ይህን የኢትዮጵያውያን እና የአንዳንድ ሀገሮች ትውፊት የሚደግፍ መረጃ በቫቲካን ጥንታዊ መዛግብት ዘንድ ማግኘታቸውን በ2011 ብሬንት ላንዳው የተባሉ በአሜሪካ ኦክላሆማ የሃይማኖት ጉዳዮች ጥናት ፕሮፌሰር ተናግረው ነበር፡፡ እንደ እርሳቸው ከሆነ ይህ በጥንታዊው የሱርስት ቋንቋ የተጻፈውና ማቴዎስ ወንጌሉን ከጻፈ በኋላ መቶ ዓመት በማይሞላ ጊዜ ውስጥ ከተጻፈ ሌላ መዝገብ የተቀዳው ጥንታዊ መጽሐፍ፣ የሰብአ ሰገልን ሀገር እና አመጣጥ ይተነትናል፡፡
መጽሐፉ ከዋናው መጽሐፍ የተገለበጠው በ8ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሲሆን ፕሮፌሰር ብሬንት ላንዳው በጉዳዩ ላይ ለሁለት ዓመታት ጥናት ማድረጋቸውን ገልጠዋል፡፡ ይህ ጥንታዊ መዝገብ ሰብአ ሰገል እንደ መጡ ለብዙ ጊዜ ሲታመንበት ከነበረው ከፋርስ ሀገራቸውን ራቅ በማድረግ የመጡት «ሺር» ከሚባል ሀገር ነው ይላል፡፡ ሺር በአሁኑ ጊዜ በቻይና ግዛት ውስጥ ይገኛል፡፡ እነዚህ የሺር ሰዎች የአዳም ልጅ የሴት የልጅ ልጆች ሲሆኑ በሀገሩ እጅግ ብዙ ጠቢባን ይኖሩ እንደ ነበር ይገልጣል፡፡
ሴት ጽፎ በሰጣቸው ትንቢት ላይ በምሥራቅ ኮከብ ሲወጣ ያን ጊዜ አምላክ በሥጋ ይገለጣልና እጅ መንሻ ይዛችሁ ሂዱ እንዳላቸው የቫቲካኑ መዝገብ ያስረዳል፡፡ ይህንን በተመለከተ የኢትዮጵያው ትውፊት መነሻውን ከሴት ያደርግና በሴም በኩል አድርጎ በፋርስ ለሚኖሩ ፈላስፋ ማኅበረሰብ ትንቢቱ መድረሱን ያትታል፡፡ በዚያም ዘረደሸት የሚባል ፈላስፋ መነሣቱን እርሱም ከምንጭ ዳር ሲፈላሰፍ ድንግል በሰሌዳ ኮከብ ተስላ ሕፃን ታቅፋ አየ ይላል፡፡ ይህንንም በሰሌዳ ቀርፆ ለልጆቹ ሰጣቸው፡፡ አላቸውም «ይህንን ኮከብ በሰማይ ስታዩ ሰማያዊ ንጉሥ ይወለዳልና ሄዳችሁ ስገዱ፣ ይህንንም እጅ መንሻ ስጡ፡፡» እነርሱም ዘመኑ ሲደርስ ኮከቡ ሲወጣ መጡ፡፡
በሌሎች ትውፊቶች ደግሞ እነዚህ ሰዎች ፋርስ እና ዓረብን ተካፍለው ይገዙ የነበሩ ነገሥታት እንጂ የፋርስ ሰዎች አይደሉም የሚል አለ፡፡ ብዙ ጊዜ ፋርስ እና ዓረብ ከምሥራቅም ከምዕራብም ያሸነፈ የሚገዛቸው አካባቢዎች ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያውያን፣ ግሪኮች፣ ሮማውያን፣ ግብፆች እየተፈራረቁ አሸንፈው ገዝተዋቸዋል፡፡
በዚያን ዘመንም ኮከብን መመልከት እና ኮከብን ማጥናት የኃያላን ነገሥታት ሁሉ ጠባይ በመሆኑ የሥነ ከዋክብት ተመራማሪዎችም ሆኑ ኮከብ ቆጣሪዎች በየቤተ መንግሥቱ ነበሩ፡፡ በናቡከደነፆርም ሆነ በፈርዖን ቤተ መንግሥት ኮከብ ቆጣሪዎችን የምናያቸው በዚህ ምክንያት ነው፡፡
እነዚህን ሰዎች በሚያውቁት ኮከብ ለመምራት እንጂ የመራቸው ኮከብ ሳይሆን መልአክ መሆኑን መተርጉማን ይናገራሉ፡፡ ለዚህም የሚያቀርቡት ማስረጃ በመጀመርያ ኮከብ በቀን ሊታይ አይችልም፣ በመቀ ጠልም ዝቅ ብሎም እነርሱ ሊያዩት በሚችሉት ደረጃ አይጓዝም የሚለውን ነው፡፡ አንዳንድ ሊቃውንትም ይህ ኮከብ በመንገድ እየመራቸው ከተማ ሲገቡ ግን ይሠወራቸው ነበር ይላሉ፡፡
በመሆኑም ሰብአ ሰገል ከተለያዩ ሀገሮች የመጡ ነገሥታት ናቸው እንጂ የፋርስ ብቻ አይደሉም የሚሉ መዛግብት አሉ፡፡ የግብጽ፣ የሶርያ፣ የአርመን እና አንዳንድ የሀገራችን መጻሕፍትም ይህንኑ ይደግፋሉ፡፡ ብዙ ጊዜ በልዩ ልዩ ሥዕሎች ሲገለጡ የሰብአ ሰገል ቁጥር ሦስት ነው፡፡ ይህም ከሰጡት ስጦታ በመነሣት የተወሰደ ነው፡፡ አንደኛው የኢትዮጵያው ትውፊት «ሲነሡ አሥራ ሁለት ሆነው መነሣታቸውን ገልጦ ኤፍራጥስ ወንዝ ሲደርሱ ዘጠኙ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሦስቱ መቀጠላቸውን» ያስረዳል፡፡ የቀሩበትንም ምክንያት ምናልባት ከኋላ ጦር ተነሥቶባቸው ወይንም ስንቅ አልቆባቸው ይሆናል ይላል፡፡
በብዙ ጥንታውያን መዛግብት የምናገኘው ግን የሦስቱን ስም ብቻ ነው፡፡ የኢትዮጵያው መዝገብ ሦስቱን «ነገሥታት ናቸው» ይልና ስማቸውን ማንቱሲማር፣ በዲዳስፋ እና ሜልኩ ይባላሉ ይላል፡፡ ሲመጡም ብቻቸውን ሳይሆን ዐሥር ዐሥር ሺ ሠራዊት አስከትለው ነበር ይላል፡፡ በታኅሳስ ሃያ ዘጠኝ የሚነበበው ስንክሳራችንም ነገሥታቱን ሦስት አድርጎ ሠራዊታቸውን አሥር አሥር ሺ ያደርሰዋል፡፡
በእስክንድርያ በ5ኛው መክዘ ከተጠናቀረ በአንድ በግሪክ ከተጻፈ መዝገብ በመውሰድ ላቲኑ ስማቸውን «ሜልክዮር፣ ካስፓር እና ባልታዛር» ያደርገዋል፡፡ አሁን ባሉት የግሪክ መዛግብት ግን «አፔልዮስ፣ አሜሪየስ እና ደማስቀስ» ተብለው ነው የሚጠሩት፡፡ የሶርያው መዝገብ ደግሞ ስማቸውን «ላርቫንዳን፣ ጉሽናሻፕ እና ሆርሚስዳስ» ነው ይላል፡፡ የአርመኑ ደግሞ «ካግጳ፣ ባዳዳካሪዳ እና ባዳዲልማ» መሆና ቸውን ያሳያል፡፡ የዕብራይስጡም «ጋልጋላት፣ ማልጋላት እና ሳራኪን» ብሎ ይጠራቸዋል፡፡
እነዚህ ሦስቱ ከያፌት፣ ከሴም እና ከካም ወገን መምጣታቸውን የግሪኩም፣ የላቲኑም፣ የግብጹም፣ የአርመኑም ሆነ የሶርያው ያትታሉ፡፡ እንደ ትውፊቱ ከሆነ ስማቸውን እና የመጡበትን ሀገር ቀጥሎ ያለው ሠንጠረዥ ያሳየናል፡፡
|
በኢትዮጵያ
|
በግሪክ
|
በላቲን
|
በአርመን
|
በዕብራይስጥ
|
የመጡበት ሀገር
|
|
ማንቱሲማር
|
አፔልዮስ
|
ሜልክዮር
|
ካግጳ
|
ጋልጋላት
|
አውሮፓ
|
|
በዲዳስፋ
|
አሜሪየስ
|
ካስፓር
|
ባዳዳካሪዳ
|
ማልጋላት
|
አፍሪካ
|
|
ሜልኩ
|
ደማስቀስ
|
ባልታዛር
|
ባዳዲልማ
|
ሳራኪን
|
እስያ
|
አንዳንድ ሊቃውንት እነዚህን አህጉር ወክለው የሄዱት ነገሥታት ከየት ቦታ እንደመጡ መረጃ ለመስጠት ሞክረዋል፡፡ ከአውሮፓ የመጣው የሴልቲክ ዘር እንደሆነ፣ ከእስያ የሄደው ከፋርስ እንደሆነ፣ የአፍሪካው ደግሞ የኢትዮጵያ ንጉሥ እንደሆነ ተገልጧል፡፡ ኢትዮጵያውያን መዛግብት በዚህ ጊዜ የነበረው የኢትዮጵያ ንጉሥ ባዚን በመሆኑ የሄደው እርሱ ነው ይላሉ፡፡ ትርጓሜ ወንጌሉ ግን ከካም ነገድ መሆኑን እንጂ ኢትዮጵያዊ መሆኑን አይገልጥም፡፡
ከሦስቱ ነገሥታት ወርቅን የአውሮፓው፣ ዕጣንን የኢትዮጵያው ከርቤን ደግሞ የእስያው መውሰዳቸው ይታመናል፡፡ ወርቅ ዘለዓለማዊ ንጉሥ መሆኑን እንደሚያሳይ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ከርቤ በዓረብ እና በሕንድ እጅግ የታወቀ ነው፡፡ እሥራኤልም ያስገቡ የነበረው ከእነዚህ ቦታዎች ነው፡፡ ከርቤ ለሕመም መድኃኒትነት እና የተሰበረን አካል ለመጠገን ይውል ነበር፡፡ ሰው ሲያርፍም ሥጋው በከርቤ ይታሽ ነበር፡፡ ሰብአ ሰገል ከርቤ ሲያቀርቡ የተሰበረውን የሰው ልጅ ለመጠገን፣ የተለያዩትን ሰው እና እግዚአብሔር አንድ ለማድረግ ሞትን ትቀምሳለህ ማለታቸው ነው ይላሉ መተርጉማኑ፡፡ ዕጣን ደግሞ ለመካከለኛው ምሥራቅ ይሄድ የነበረው ከኢትዮጵያ ነው፡፡ ዕጣን በካህናት እጅ ይቀርብ የነበረ መሥዋዕት ነው፡፡ አንተ ዘለዓለማዊ ካህን ሆነህ ሠውተህም ተሠውተህም ታድናለህ ማለታቸው ነው፡፡
በዚህ የተነሣ በአውሮፓ ቤተ መቅደሶች በተሳሉ የሰብአ ሰገል ሥዕሎች ውስጥ አንዱን ኢትዮጵያ አድርጎ መሳል የተለመደ ነው፡፡
የሰብአ ሰገልን ፍጻሜ በተመለከተ ልዩ ልዩ አመለካከቶች አሉ፡፡ ምንም እንኳን ክርስቶስን አግኝተው ደስ ብሏቸው ቢመለሱ ክርስቲያን የሆኑት ግን ዘግይተው መሆኑ ይነገራል፡፡ የሀገራችን መዛግብት ሐዋርያው ናትናኤል አስተምሮ እንዳጠመቃቸው ሲገልጡ የሶርያ መዛግብት ግን ቶማስ ወደ ሕንድ ሲጓዝ አስተምሮ እንዳጠመቃቸው ይናገራሉ፡፡
ማርኮ ፖሎ የተባለው አሳሽ በ1270 በዛሬዋ ኢራን ከቴህራን በስተ ደቡብ ሳቬህ በሚባል ሥፈራ የሰብአ ሰገልን መቃብር ማየቱን ይገልጣል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ዕሌኒ ንግሥት ወደ ኢየሩሳሌም በ4ኛው መክዘ በሄደች ጊዜ ይዛው ወደ ቁስጥንጥንያ የመጣች፣ በኋላም በሐጊያ ሶፍያ ቤተ ክርስቲያን ያስቀመጠቺው፣ በመጨረሻም ወደ ሚላን የተዛወረውና በ1164 ዓም በፍሬደሪክ አንደኛ ትእዛዝ ወደ ኮሎኝ ካቴድራል እንደ ገባ የሚታመን የሰብአ ሰገል ዐጽም አለ፡፡
በርግጥ በተለያዩ ጥንታውያን የክርስቲያን ሀገሮች ሁሉ የሰብአ ሰገል ታሪክ የታወቀ እና አያሌ መዛግብት ያሉት፣ በብዙ ጥንታውያን ሥዕሎችም የተገለጠ ነው፡፡ በኢትዮጵያ በየመጻሕፍቱ ውስጥ እየገባ እንጂ ራሱን የቻለ ታሪክ አላገኘሁለትም፡፡ ምናልባት መዝገቦቻችንን በደንብ ብናገላብጥ ግን የተሻለ መረጃ ልናገኝ እንችል ይሆናል፡፡
ከአቡዳቢ
© ይህ ጽሑፍ በሮዝ አሳታሚ ኃ. የተወሰነ የግ.ማ በሚታተመው “አዲስ ጉዳይ መጽሔት” ላይ ያወጣኹት ነው። ጽሑፎቹን በድጋሚ በመጽሔት፣ በጋዜጣ ወይም በተመሳሳይ የሕትመት ውጤት ላይ ማተም አይገባም።
