ሸሪፍና ሻርማርኬ ተፋጠዋል

በሶማሊያ የሽግግር መንግስት ፕሬዝዳንት ሸሪፍ ሼክ አህመድና በጠቅላይ ሚኒስትር ኦማር አብድረሺድ ሻርማርኬ መኃል የተፈጠረው አለመግባባት ተካሯል። ምናልባት ደካማው የሽግግር መንግስት ሊለይለት ይችላል ተብሏል።

የሶማሊያ የሽግግር መንግስት በዚህም በዚያም ተወጥሯል። የመሪዎቹ ሽኩቻ ምናልባትም ከአልሸባብ ጥቃት የበለጠ ደካማውን የሽግግር መንግስት ሊያጠፋ እንደሚችል ተሰግቷል። በእርግጥም ሽሪፍና ሸርማርኬ አደባባይ የወጣ ጸብ ገጥመዋል። እስከአሁንም ለገላጋይ አስቸግረዋል። አንዱ አንደኛው ላይ ጣት ይጠነቁላል። ይወነጅላል። የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ጋዜጠኛ ሙስጠፋ ሀጂ አብዲኑር እንደሚለው ግን የሁለቱ መሪዎች ጸብ ምክንያት በግልጽ አይታወቅም። «ግልጽ አይደለም። በሁለቱ መሪዎች መኃል የተፈጠረው ችግር መሰረታዊ ምክንያቱ ምን እንደሆነ በትክክል አይታወቅም። ግን አንዳንድ ምንጮች እንደሚሉት ሁለቱ መሪዎች በአደባባይ እርስ በእርስ መወራረፍ ከጀመሩ ቆይተዋል። የሶማሊያ ብጥብጥ ከቁጥጥር ውጪ መሆኑ፤ አንዱ አንደኛው ላይ ማላከክ፤ ጥፋተኛ አድርጎ መኮነንን ይዘዋል። ፕሬዝዳንቱ የሚሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሃገሪቱን ደህንነት ማስጠበቅ አልቻሉም። አቅሙም የላቸውም–ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ደግሞ ፕሬዝዳንቱ ለቦታው የሚመጥኑ አይደሉም ይላሉ። እስካሁን ስለሁለቱ መሪዎቹ ችግር የተረዳነው ይህንን ነው።»

[podcast]http://dw-world-od.streamfarm.net/Events/dwelle/dalet/mp3/amh/0120a801.mp3[/podcast]