አርቲስት ሰብለ ተፈራ በመኪና አደጋ ህይወቷ አለፈ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 1፣ 2008 (ኤፍ.ቢ.ሲ) አርቲስት ሰብለ ተፈራ አዲስ አበባ ውስጥ ዛሬ 8 ሰዓት አካባቢ ከጎተራ ወደ ሳሪስ ጎዞ ስታደርግ ንፋስ ስልክ ቀለም ፋብሪካ አካባቢ በደረሰባት የመኪና አደጋ ህይወቷ አልፏል።
የአደጋ መርማሪውን ዋቢ አድርገው የአዲስ አበባ ፖሊስ ፖሚሽን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ምክትል ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ እንዳሉት፥ የትዳር አጋሯ አርቲስት ሰብለን ከጎኑ አድርጎ እያሽከረከራት የነበረችው ቪትዝ መኪና በተጠቀሰው አካባቢ በሚገኝ ቁልቁለታማ ቦታ ከቆመ ሌላ ተሽከርካሪ ጋር በመጋጨቷ ነው አደጋው የተከሰተው።
መኪናዋ ተፈናጥራ በድጋሚ የቆመውን መኪና መግጨቷ አደጋውን የከፋ እንዲሆን እድርጎታል።
አርቲስት ሰብለ በወቅቱ ክፉኛ በመጎዳቷ ወዲያውኑ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ዘንባባ ሆስፒታል የህክምና እርዳታ ቢደረግላትም ህይወቷ ሊተርፍ አልቻለም።
ሞገስ የተሰኘው ባለቤቷ በአደጋው የከፋ ጉዳት እንዳልደረሰበትም ነው የተገለፀው።
አርቲስት ሰብለ በተለይም በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በተከታታይ ሲቀርብ በነበረው የ “ትንንሽ ፀሃዮች” ድራማ “የእማማ ጨቤ”ን ገፀ-ባህርይ በመላበስ ተወዳጅነትን አትርፋለች።
በተጨማሪም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ቅዳሜ ምሽት እየተላለፈ በሚገኘው “ቤቶች” ተከታታይ ድራማ ላይ “ትርፌ” በተሰኘው ገፀ-ባህርይ ትታወቃለች።
ሰብለ በተለያዩ ፊልሞች እና ተውኔቶች ላይ በመተወንም ተወዳጅነትን ካተረፉ ወጣት አርቲስቶቻችን ተጠቃሽ ናት።
በጥላሁን ካሳ