የወያኔ የመሬት ሊዝ አዋጅና የይዞታ ባለቤትነት

(Reporter) — የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር መስከረም 30 ቀን 2004 ዓ.ም. የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ በወጣው አዋጅ ዙርያ ትናንት ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥቷል፡፡

መግለጫውን የሰጡት ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ደሳለኝ አምባውና በሚኒስቴሩ የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ እስራኤል ተስፋዬ ናቸው፡፡ አዋጁን በተመለከተ በተለይ አቶ እስራኤል ለጋዜጠኞች ከሰጡት ማብራርያ የተወሰነውን ዝርዝር ከዚህ በታች ይመልከቱ፡፡

ቀደም ሲል የነበረው አዋጅ 272/94 ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት ሥራ ላይ ውሏል፡፡ እንደምታውቁት መሬት የከተሞች ብቸኛ ሀብት ነው፡፡ ይህንን ብቸኛ ሀብት በአግባቡ ለማስተዳደር በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ አዋጆች ወጥተዋል፡፡ የእነዚህ አዋጆች አካል የሆነው አዋጅ ቁጥር 272 በሥራ ላይ በነበረበት ጊዜ አዋጁ ሲወጣ ያላያቸው ከፍተኛ ክፍተቶችና ችግሮች ተከስተዋል፡፡ እንዲሁም መሬትን የተሻለ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዲኖረው ለማስቻል የተሻለ አሠራር መፍጠር አስፈልጓል፡፡

ይህ ሥርዓት ካልተፈጠረ በተለይ በከተማ መሬት ላይ ትልቅ ችግርና የኪራይ ሰብሳቢነት አደጋ ነው የሚኖረው፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ዓመታት የታየውን ችግር ለመፍታት በመጀመርያ የዳሰሳ ጥናት ተደርጓል፡፡ ጥናቱ በመሬት ላይ በተጨባጭ ያሉ ችግሮችን የለየ ነው፡፡ ከዚህ ጥናት ተነስተን ወደ ፖሊሲው ነው የገባነው፡፡ የፖሊሲው አቅጣጫ መሬት ላይ ወጥ የሆነ ልማትና ማኔጅመንት እንዲኖር የሚያስችል ነው፡፡ እነዚህን ችግሮች በፖሊሲው ምላሽ ተሰጥቶ ወደ ሕግ አግባብ መጥቷል ማለት ነው፡፡ እንደአብነት ከነበሩት ችግሮች አንዱ ክፍተት፣ መሬት ላይ ምንም ዓይነት ግንባታ ሲያካሂዱ ወይም ከደረጃ በታች የሆነ ግንባታ በማካሄድ ለሦስተኛ ወገን ማስተላለፍ ነው፡፡

ከዚህ ግብይት መንግሥት ሊያገኝ የሚገባው ጥቅም በግለሰቦች ኪስ ውስጥ እንዲገባ ሆኗል፡፡ በዚህ ዘርፍ ትልቅ የኪራይ ሰብሳቢነት አደጋ ነው የተፈጠረው፡፡ ይህ ማለት ባዶ መሬትን፣ ለልማት ሊውል የሚችል መሬትን፣ ወቅት ጠብቆና አጥሮ ይዞ ከዚያ በኋላ በጊዜ ሒደት ምንም ዓይነት እሴት ሳይጨመር በማስተላለፍ ብቻ፣ አላግባብ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ወደተወሰኑ ግለሰቦች ኪስ እየገባ የንብረት ልውውጡን ገበያ አናግቷል፡፡

ሌላው ትንሽ መሠረት ተጥሎና መሠረት የጣለበትን ቦታ በመሸጥ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብም ሲታፈስ ቆይቷል፡፡ ይኼ የራሱ የሆነ ትልቅ ችግር ነው፡፡ ሌላው በዚህ አዋጅ የነበረው አንዱ ከተሞች በጊዜ ሒደት ወደ ሊዝ ሥርዓት ይሸጋገራሉ ይላል፡፡ ሆኖም ግን የአዋጅን መንፈስ ተከትሎ ወደ ሊዝ የማሸጋገር ሒደቱ ከክልል ክልል፣ ከከተሞች ከተሞች ወጣ ገባ ነው የሆነው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ 150 ከተሞች ብቻ ናቸው በሊዝ ሥርዓት መሬት በማስተላለፍ ላይ ያሉት፡፡ ይኼ ማለት በሊዝ ሥርዓት ቦታ ማስተላለፍ ማለትና አሁን ያለውን ነባር ይዞታን ወደ ሊዝ ማስተላለፍ የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ በሊዝ አግባብ ቦታ ማስተላለፍ ማለት መንግሥት መሬት ላይ የመሠረተ ልማት አሟልቶ ማስተላለፍ ማለት ነው፡፡ ይኼ እንግዲህ በአገር አቀፍ ደረጃ 950 ከተሞች አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 150 ናቸው ይህንን የሚገለገሉበት፡፡ የሊዝ ሥርዓቱ ካለው ጠቀሜታ አንፃር ወደ ሊዝ ሥሪት ማስገባቱ ዘግይቷል፡፡ ይህንን ማስተካከል አስፈልጓል፡፡

ሌላው የመሬት አሰጣጥ ስልቱ በጣም ወጣ ገባ ነው፡፡ የቀድሞ አዋጅ ከድርድር ጀምሮ አምስት ያህል ቦታ የሚሰጥበት ስልት ነበረው፡፡ እነዚህ ስልቶች ወደታች ሲወርዱ አፈጻጸማቸውም ይለያያል፡፡ ከድርድር ጀምሮ በዕጣ፣ በሽልማት፣ በምደባና በጨረታ ቦታ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ የስልቶቹ አተገባበር የተለያየ ነበር፡፡ ይህንን ሁኔታ ወጥ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ግልጽ በሆነ መንገድ ስልቱን ማስተካከል ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ በመነሳት በአዋጁ ሁሉም ክፍል ላይ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡ አንደኛ የመሬት አስተዳደርና ልማት ሥርዓቱ ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖር ማስቻል ነው፡፡ በጣም ግልጽ ተጠያቂነት ያለበት አሠራር ለማስፈን አዲሱን አዋጅ ቁጥር 272/2004 ማውጣት አስፈልጓል፡፡ አዋጁ አምስት ክፍሎችንና 37 አንቀጾችን ይዞ ወጥቷል፡፡ በስፋት በመሬት ላይ ትኩረት አድርጎና እንዲስተካከል በሚያደርግ መልኩ ተቀርጿል፡፡

አዋጁ ከፍተኛ ውዥንብርና ስጋት በኅብረተሰቡና በቤተሰብ ውስጥ አምጥቷል
አዋጁ መስከረም 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ነው የፀደቀው፡፡ ከዚያ ጊዜ በኋላ በኅብረተሰቡ ውስጥ ለማስረፅ የተወሰነ ጊዜ ወስዷል፡፡ ይኼንን አዋጅ በአግባቡ ማስረዳት ይጠበቃል፡፡ በቀጣይም የምንሄድበት ጉዳይ ነው፡፡ በሊዝ አዋጁ ስጋት የሚፈጥር ምንም ነገር እንደሌለ ነው እኔ የምገነዘበው፡፡ በተለይ ሽያጭን በተመለከተ፡፡ ካነሳችሁት ጥያቄ አንፃር ለምሳሌ አንድ ሰው ይዞታውን ይሸጣል፡፡ የተሸጠውን ይዞታ ሲያስተላልፍ ወደ ሊዝ ሥሪት ይገባል፡፡ ይህ እንግዲህ በቤተሰብ መካከል የተለያየ አምባጓሮ እየፈጠረ ነው፡፡ ይህ የሚፈጸመው ነባር ሥሪት ላይ ያለ ንብረት ለመሸጥ የሚከላከል ነገር የለም፡፡ ይሸጣል፡፡ ሲሸጥ ግን እንደምታውቁት መሬት በዚህች አገር የሕዝብና የመንግሥት ሀብት ነው፡፡ ንብረቱ በሚሸጥበት ጊዜ በተገኘው ዋጋ ይሸጣል፡፡ ይኼ የመሬት ዋጋ ነው? ይኼ የቤቱ ዋጋ ነው? አይለይም፡፡ እንዲሁ ይሸጣል፡፡ ነገር ግን ለስም ዝውውር በሚመጣበት ጊዜ የስም ዝውውሩ የሚደረገው በሊዝ አግባብ ነው የሚሆነው፡፡ በሊዝ አግባብ ሲዛወር አንዱ መነሻ ዋጋውን መሠረት አድርጎ ነው፡፡ ይህ መነሻ ዋጋ እንግዲህ አዲስ አበባ በየትኛውም ቦታ ብትሄዱ መነሻ ዋጋው ከ600 ብር አይበልጥም፡፡

ለምሳሌ አንድ ሰው በ200 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያለ ንብረቱን ሲሸጥ ይህ ቦታ የሚገኝበት አካባቢ ያለው መነሻ ዋጋ በካሬ ሜትር 500 ብር ቢሆን 200 ሲባዛ በ500 ይሆናል 100 ሺሕ ብር ነው፡፡ የሊዝ ዋጋው 100 ሺሕ ብር ነው ማለት ነው፡፡ በሊዝ ውል ላይ በተቀመጠው መሠረት ከዚህ ገንዘብ ላይ 10 በመቶ ነው የሚከፍለው ወደ ስም ዝውውር ሲገባ፡፡ ይህንን ይከፍልና ቀሪውን ዘጠና በመቶ በሊዝ ውል በተቀመጠው መሠረት በ30 ወይም በ40 ዓመት አጠናቆ ይጨርሳል ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት አንደኛ ይህ መሬት ለገዢው አካል ዋጋ (ቫሊዩ) እንዲኖረው ያደርገዋል፡፡ የሊዝ ዋጋ ይኖረዋል፤ የሊዝ ዋጋ የሚሰጣቸው መብቶችና ጥቅሞች አሉ፡፡ ከነባር ይዞታ ይልቅ፡፡ አሁን ይህ ዋጋ በዋስትና ለማስያዝና በከፈለው መጠን እዚያው ላይ ባለው መጠን በዋስትና ለማስያዝና ተጠቃሚ ለመሆን ያስችላል፡፡ ሁለተኛ አንዴ ውል ሲገባ 30 ዓመትም ይሁን 40 ዓመት ውል በገባበት ወቅት ከሚከፍለው የሊዝ ክፍያ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ በነበረው ነባር የይዞታ ሥርዓት ቢሆን ሰውየው የሚከፍለው በየወቅቱ በሚከለሰው ግብር ነው፡፡ በየዓመቱ ሊጨምር ይችላል፡፡

በየወቅቱ የማይጨመር ክፍያ ነው በየጊዜው ለሊዝ ኪራይ የሚከፍለው፡፡ ሁለተኛ ለሕዝብ ጥቅም ተብሎ ከቦታው ላይ ሲነሳ ተመሳሳይ ስፋትና ደረጃ ባለው ቦታ ላይ ነው ልዋጭ የሚሰጠው፡፡ ስለዚህ ጥቅሙ ያለው ወደ ሊዝ የተሸጋገረለት ሰው ነው፡፡ ይህ ሲታይ መንግሥት ቀደም ሲል መረጃዎች ላይ ካያችሁ የመሬት ዋጋ ይህን ያህል የሚል አለው፡፡ የንብረቱ ይህንን ያህል የሚል አለው ከዚያ ያቺ የተተመነችውን ነው የሚከፍለው፡፡ ይህ ተተምኖ ነው ክፍያ የሚፈጸመው፡፡ ቀድሞ ሲከፈል የነበረው አሹራ በአዲሱ አዋጅ ወደ ሊዝ ሲዞር በሊዝ ክፍያ ይተካል፡፡ ይህ ማለት በጣም ኢምንት የሆነ ክፍያ ነው የሚከፍለው፡፡ ስለዚህ በግለሰቦች ላይ የሚያመጣው ተፅዕኖ የለም፡፡

በውርስ የተገኘ ይዞታ
የግል ባለይዞታ ሆነው በውርስ ከአንድ ሺሕ እስከ አንድ ሺሕ አምስት መቶ ካሬ ሜትር ወይም ሰፋ ያለ ይዞታ በውርስ ያገኙ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ በውርስ ያገኙ ሰዎች ቦታውን በውርስ ያገኙ በመሆኑ አዋጁም ከውርስ በስተቀር ስለሚል አይከፍሉም፡፡ በሌሎች ክፍለ ከተሞች ደግሞ ይከፍላሉ አሠራሩ ወጥ አይደለም የሚባል ነገር አለ፡፡ ለነገሩ አሁን ባለው ሁኔታ አዋጁ ተግባራዊ አልተደረገም፡፡ የሽግግር ጊዜ ተቀምጦለታል፡፡ ስለዚህ አሁን ባለው ሁኔታ ክፍለ ከተሞች አንተ ትከፍላለህ አንተ አትከፍልም የሚያስብል ነገር የለም፡፡ አዋጁ ሦስት ወር የሽግግር ጊዜ አስቀምጧል፡፡ በዚህ አግባብ ላይ ያለ ውርስ የቀረበበት ምክንያት ምንድን ነው? ለውርስ የማይከፈልበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚሉ ነገሮን ማየት ተገቢ ነው፡፡ አንዱ ውርስ ሲሆን ‹‹ኖርማል ትራንዛክሽን›› አይደለም የሚፈጸመው፡፡ የፍትሐ ብሔር ሕጉ ውርሱ ለሚገባቸው አካላት ነው ይዞታው የሚተላለፈው ይላል፡፡ ይህ መብት ያላቸው አካላት ደግሞ ትራንዛክሽን ውስጥ ለመግባት ያላቸው የኢኮኖሚ ሁኔታ ዝግጁ ካለመሆኑ አንፃር ትራንዛክሽን ሊፈጸም አይችልም፡፡ በመሆኑም መብታቸው መተላለፍ ካለበት ተነጣጥሎ መቅረት የለበትም ስለዚህ እንዲተላለፍላቸው ይደረጋል፡፡ ግን በቀጣይ እነዚህም ቢሆኑ በሚጠናው ጥናት መሠረት ከኅብረተሰቡ ጋር ውይይት ተደርጎ በቀጣይ ከነባር ይዞታ ሥሪት ወደ ሊዝ ሥሪት በሚሸጋገርበት ጊዜ የሚፈጸም ነው የሚሆነው፡፡ በጥናቱ ይህንን ያህል ካሬ ቦታ ያለው ሰው ምን ያህል ይከፍላል የሚል ቀጣይ አጠቃላይ ጥናት ተደርጎ መልስ የሚሰጥበት ይሆናል፡፡

የባዶ መሬት ሽያጭ
አንድ መንግሥት በሊዝ አግባብ ቦታ ሲሰጥ ቦታው ቀጥታ ለልማት ውሎ፣ የሥራ ዕድል ፈጥሮ፣ ኢኮኖሚውን አሳድጎ፣ ሌሎች ተጨማሪ ጥቅሞችን እንዲያመጣ ነው፡፡ ባዶ መሬት እንዲገላበጥ አይደለም የመንግሥት ፍላጎት፡፡ ይሁንና ግን እነዚህ መጠነኛ ግንባታ የገነቡ ሰዎች ግንባታውን ለመቀጠል አቅም ሊያጥራቸው ይችላል፡፡ በተወሰነ ደረጃ ላይ የተወሰነ የአቅም ማነስ ተፈጥሮ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ በሚሆን ጊዜ አዋጁ በግልጽ አስቀምጧል፡፡ ሰውየው መብቱን ማስተላለፍ ይችላል፡፡ አይደለም ግንባታ ከግማሽ በታች አከናውኖ ይቅርና የግንባታ ዘመኑ እስካላለፈ ድረስ ባዶ መሬትም ማስተላለፍ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ይህንን ይዞታ ሲያስተላልፍ ይህ ሰው በዚያ ቦታ ላይ ያለው ዋጋ፣ የመሠረተ ልማት፣ የግብይት ዋጋ ከፍ ማለት፣ ጥቅሞች የተገኙት በመንግሥት በተካሄዱ ሥራዎች እንጂ ሰውየው የሠራቸው አይደሉም፡፡ ለውጡ የመጣው ከተሞች መሠረተ ልማት ዘርግተው ሀብታቸውን አፍሰው ባመጡት ጥቅም ነው፡፡

ሻጩ ቦታውን ሲያስተላልፍ የንብረቱን ዋጋ ማለትም ለሊዝ የከፈለውን ቅድመ ክፍያ ማግኘት ይችላል፡፡ ይህ ገንዘብ በባንክ ቢቀመጥ ወለድም ያገኛል፡፡ ከተገኘው የመሬት ዋጋ ልዩነቱን አምስት በመቶ ያህሉን ይሰጠዋል፡፡ ለለፋበት ወዲህ ወዲያ ላለበት ማለት ነው፡፡ በዚህ አግባብ ክፍያው ይፈጸማል፡፡ የሚተላለፍለት ግለሰብ ግን የሊዝ ውሉን ቀደም ሲል በ18 ወር ይጠናቀቃል ተብሎ ውል ከተፈጸመ አዲሱ ውል ተቀባይም በዚህ ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ እርግጠኛ መሆን ይኖርበታል፡፡ ነባር ይዞታን ወደ ሊዝ ሥሪት ሲገባ ይኼ አዋጅ ላይ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ ነባር ይዞታ ወደ ሊዝ በሚሸጋገርበት ጊዜ ጥናት ተደርጎ ነው፡፡ አራት ዓመት የተሰጠው ለጥናት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ጥናት ተደርጎ ከኅብረተሰቡ ጋር በቂ ውይይት ተደርጎበት ወደ ሊዝ ሥርዓት የሚሸጋገርበት አግባብ ይኖራል፡፡ ወደ ሊዝ ሲሸጋገር በመነሻ ዋጋ ነው የሚተላለፈው፡፡ ነገር ግን ይህንን ጥናት ሳይጠብቅ የሚሸጋገሩ ነገሮች ተለይተው ተቀምጠዋል፡፡ አንዱ በትራንዛክሽን ጊዜ ይህ ጥናት ሳይጠበቅ ወደ ሊዝ እንዲገባ ይደረጋል፡፡

ሁለተኛው በሕገወጥ አግባባ የየተያዘ መሬት ሕጋዊ እንዲሆን ከተሞች ሲወስኑ ቀድሞ በዚያ መሬት የተከፈለ ነገር የለም፤ አግባብ በሆነ አካል የተሰጠ ቦታም አይደለም፡፡ ከተሞች ይህንን ቦታ ወደ ሊዝ ሥርዓት እንዲገባ ሲያደርጉ በሊዝ አግባብ ይሆናል፡፡ ሌላው ሁለት ይዞታዎች ሲቀላቀሉ ሊዝ ይሆናል፡፡ ማለትም አንድ ሰው ነባር ይዞታ አለው፡፡ እዚያ አጠገብ ቦታ በሊዝ ቢገዛና መቀላቀል ካሰበ ቦታው በሊዝ ሥሪት ይገባል፡፡ እንዲሁ እንዲቀጥል ከፈለገ ይዞታው ወደ ሊዝ ሳይገባ ይቀጥልበታል፡፡ ይቀላቀል ሲል ነው ወደ ሊዝ ሥሪት የሚገባው፡፡ ሰውየው ለነባር ይዞታው የሚከፍለው በአካባቢው የቦታ መነሻ ዋጋ ይሆናል፡፡ ካርታው አንድ ላይ ይዘጋጅለታል፡፡ ከዚያ ወደ ውል ይኬዳል፡፡ በሚወጣው ደንብ ላይ በደንብ የሚዘረዘሩ ነገሮች ይኖራሉ፡፡

የሊዝ ዘመን ዕድሳት
አዋጁ ሊዝ ሊታደስ በማይችልበት ሁኔታ ካሳ አይከፈልም ይላል፡፡ ሊዝ የማይታደስበት ሁኔታ አለ ወይ? እንግዲህ ለአንድ የሊዝ ዘመን ለመኖርያ ቤት ለምሳሌ በሊዝ ቦታ ተወስዷል፡፡ ካርታው ቢታይ ለ99 ዓመት የሊዝ ዘመን ይላል፡፡ ለንግድም ሆነ ለሁሉም የሊዝ ዘመን ተቀምጧል፡፡ ይህን ወስዶ ልማቱን እየፈጸመ ሲኖር ቆይቶ 89 ዓመት ይደርሳል፡፡ አዋጁ እንደሚለው ከ10 ዓመት በፊት ለሊዝ ዕድሳት ማመልከት ስላለበት እዚህ ዘመን ላይ ሲደርስ ይታደሳልኝ ብሎ ይቀርባል፡፡ በሚቀርብበት ጊዜ እንግዲህ በ100 ዓመት ዕድሜ የአንድ ከተማን ዕድገት ማሰብ ትችላላችሁ፡፡ በአዲስ አበባ አይደለም በመቶ ዓመት ባለፉት 10 እና 20 ዓመታት የመጣውን ለውጥ ታስተውላላችሁ፡፡

ከዚህ ለውጥ ተነስቶ ያ ቦታ በሚጠናው ማስተር ፕላን መሠረት አሥር ዓመት ለማስተር ፕላን የተሰጠው ዕድሜ ነው፡፡ በማስተር ፕላኑ መሠረት ቦታው ለሌላ ልማት እንዲውል ነው የተወሰነው እንበል፡፡ በማስተር ፕላኑ ከዚያ በኋላ ይኼ ቦታ አይታደስም፡፡ በቀጣይ ሌላ ልማት ነው የሚካሄድበት ተብሎ ተወስኗል፡፡ ስለዚህ ካሳ አያገኝም ማለት ነው፡፡ ካሳ የማያገኘው በሊዝ የተሰጠ መሬት መቶ ዓመት ካገለገለ በኋላ ካሳ አይገባውም፡፡ አይደለም አንድ መሬት አንድ አገር ለምሳሌ ታይላንድን ውሰዱ እንግሊዞች በሊዝ ወስደው ገነቡ፡፡ ከ90-100 ዓመት ኖሩ፡፡ የሊዝ ዘመኑ ሲጠናቀቅ ወጡ ማለት ነው፡፡ አንድ የተከፈለ ካሳ የለም፡፡ በተሰጣቸው የሊዝ ዘመን ተጠቅመዋል፡፡ ግለሰቡ የሚገባውን ተጠቅሟል ተብሎ ነው የሚታመነው፡፡ ስለዚህ ካሳ አይገባውም፡፡ ንብረቱን ማንሳት ብቻ ነው፡፡

በምደባ ቦታ ስለመስጠት
ተተኪ ቤት ማግኘት የማይቻል ሲሆን ለምሳሌ መልሶ ማልማት ቦታ ላይ ተከራዮች አሉ፡፡ ከቀበሌ ከመንግሥት የተከራየ አለ፡፡ የመጀመርያው የሚሆነው ኮንዶሚኒየም በሚገነባባቸው ከተሞች ኮንዶሚኒየም እንዲያገኙ ማስቻል ነው፡፡ በአዲስ አበባ እየተፈጸመ ነው፡፡ ኮንዶሚኒየም በማይገነባባቸው ከተሞች ግን እነዚህ ተነሺዎች እንዲደራጁ ተደርጎ በሚያስቀምጡት የገንዘብ መጠን፣ እዚህ ላይ ሰውየው ቁርጠኛ ሆኖ ገንዘብ ማጠራቀም አለበት፡፡ ሲያጠራቅም 60 በመቶውን መንግሥት ያበድረዋል፡፡ ቦታውን ያለማል፡፡ 40 በመቶ ገንዘብ አስቀምጦ ማልማት ካልቻለ ወይም ካልፈለገ ሦስት በመቶ ተቀጥቶ ገንዘቡን [ያስቀመጠውን] ይወሰዳል፡፡ ምንም የሌለው ከሆነስ? ምንም የሌለው ከሆነ በተለያዩ የመልሶ ማልማት ቦታዎች ላይ እንደሚደረገው ተለዋጭ የቀበሌ ቤት ይሰጠዋል፡፡

ነባር ይዞታ ወደ ሊዝ ሲገባ ሕገ መንግሥቱ ያስቀመጠውን ንብረት የማፍራት ዋስትና አይጥስም?
በሊዝ በወሰደው መሬት ላይ ንብረት ማፍራትና በነባር ይዞታ ላይ ንብረት ማፍራት የትኛው ነው ለአልሚው ጥቅም ያለው? ይህ አዋጅ ሕገ መንግሥቱ ያስቀመጠውን ነው ይዞ የሄደው፡፡ ሊዝ ሲሆን ይህ መብት ይሸረፋል ወይ ነው? ሊዝ ሲሆን እንዲያውም የተሻለ ተጠቃሚ ያደርገዋል እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ በሊዝ ሥርዓት ያውም ገና ጥናቱ ተጠናቆ ከአራት ዓመት በኋላ የሚወሰን ውሳኔ ነው፡፡ እሱም ሆኖ ሳያበቃ አሠራሩ ንብረት የማፍራትን መብትን ያጠናክረዋል እንጂ የሚሸረሽርበት አግባብ የለውም፡፡ አንድ ሰው ንብረት ሲያፈራ በዋስትና እንዲያዝለት የማድረግም ጭምር ነው፡፡ ንብረት ማፍራት ብቻውን ምንም አይደለም፡፡ ንብረት ማፍራት ዋስትና ሲኖረው ነው ጥቅም ያለው፡፡ ይኼ አዋጅ ምንድን ነው ያደረገው? ይህ ንብረት ወደሊዝ ሲመጣ የሊዝ ዋስትናን ነው የሚያጎናጽፈው፡፡ ስለዚህ ዋስትናው በተጠናከረ ሁኔታ ከመሬቱና ከንብረቱ ጋር ባለበት ሁኔታ ይቀጥልለታል፡፡ የመያዣ ዋስትናው ይጠናከርለታል፡፡ ከዚሁ ጋር በተለይ ከማይንቀሳቀስ ንብረት ምዝገባ ጋር የሚመጡ አሠራሮች ይኖራሉ፡፡ ይህን ሁኔታ የበለጠ ያጠናክርለታል፡፡ መብቱን ሰፋ ያደርግለታል፡፡ ወደ ሊዝ ሲገባ መብቱ ከመሸርሸር ይልቅ እንዲያውም ይጠናከራል፡፡ በነባሩም ይዞታ ይህ መብት የተሸራረፈበት ሁኔታ የለም፡፡ ተጠናክሮ ነው ያለው፡፡ በሊዝ ሥሪት ደግሞ ሀብት የማፍራት ጉዳይ የበለጠ ዋስትና ይኖረዋል፡፡