ሰበር ዜና – በመቀሌ የሚደረገውን ሰላማዊ ሰልፍ ለማደናቀፍ መንግስት እየሞከረ ሲሆን በሌላ በኩል በአርባምንጭና ወላይታ ቅስቀሳው ቀጥሏል

በመቀሌ የሚደረገውን ሰላማዊ ሰልፍ ለማደናቀፍ መንግስት እየሞከረ ነው

በመቀሌ ከተማ የፊታችን እሑድ ሐምሌ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ለሚደረገው ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ የአንድነት ከፍተኛ አመራር አቶ የማነ አበራ ስልክ ተቀምተዋል፡፡ የመቀሌ የፀጥታ ኃይሎችና ደህንነቶች ከአቶ የማነ ከቀሙት ስልክ ላይ የተመዘገቡ የግል አድራሻዎች መዝግበው ሰጥተዋቸዋል፡፡ አመራሩ ለሰላማዊ ሰላፍ ቅስቀሳና ማስተባበር ስራ ወደስፍራው ያቀኑ ሲሆን የከተማው የፀጥታ ኃይሎችና ደህንነቶች ግን በ24 ሰዓት ውስጥ መቀሌን ለቀው ካልወጡ እርምጃ እንደሚወሰድባቸው መዛታቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ይሁን እንጂ አመራሩ በመቀሌ ከሚገኙ የአንድነት ፓርቲ አመራሮቸና አባላት ጋር አሁንም የቅስቀሳ ስራውን እያከናወኑ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተያያዘ ዜና ደግሞ በወላይታ ሶዶ ደህንነቶች የአንድነት ፓርቲ አባላት ወረቀት እንዳይበትኑ እየተከለከሉ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ህዝቡ ህዝባዊ ስብሰባው ላይ ለመሳተፍ ህዝቡ ከፍተኛ ተነሳሽነት እያሳየ እና ቅስቀሳውንም በጋራ እየሰሩ መሆኑ ታውቋል፡፡

እንዲሁም በአርባምንጭ ከተማ ሐምሌ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ለሚደረገው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የአንድነት ፓርቲ አባላትና የከተማው ነዋሪዎች ቅስቀሳ መጀመራቸውን ምንጮቻችን ከስፍራው በተለይ ለፍኖተ ነፃነት ገልፀዋል፡፡ በዚህ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የከተማው ነዋሪዎች በበኩላቸው ለሰላማዊ ሰልፉ ቅስቀሳውን ከአንድነት ፓርቲ አባላት ጋር በጋራ እየሰራን ነው ሲል ገልፀውልናል፡፡