ዝክረ የዳንኤል ክብረት እይታዎች (፫ኛ ዓመት)
ኃ/ገብርኤል ከአራት ኪሎ
ሰላምና ጤናን የምመኝላችሁ፣ በሀገር ውስጥም በውጪም የምትገኙ የዚህ ጡመራ መድረክ እድምተኞች እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ሚያዝያ ፭ ፳፻፭ ዓ.ም ነው የዳንኤል ክብረት እይታዎች በጡመራ መድረክ ላይ መውጣት የጀመሩበትን ፫ኛ ዓመት የሚዘከርበት ቀን። ከሀገር ውጪ እና በሀገር ውስጥም ሆናችሁ በተለያዩ ምክንያቶች ይህንን ፕሮግራም ላልታደማችሁ ሁሉ ስለ ነበረው ክንውን አጠር አድርጌ ላስቃኛችሁ ወደድኩኝ። መልካም ንባብ።
እንደ ልማዴ ከ፬ኪሎ የ፳፪ን ታክሲ ተሳፈርኩኝና ጉዞ ወደ አክሱም ሆቴል ሆነ። ሆቴሉ ስደርስ ሰዓቴን ተመለከትኩኝ ልክ ፮፡፵፭ ይላል። በትክክለኛው ሰዓት በመድረሴ በመደሰት ፍተሻውን አልፌ ወደ ስብሰባው አዳራሽ አቅጣጫ ጠቋሚ በሆኑ እና ጎድግዳ ላይ በተለጠፉ ጽሑፎች አማካኝነት ፎቁን ወጣሁ። ሁለተኛ ፎቅ ላይ የሚገኘው የስብሰባ አዳራሽ ስደርስ የተወሰኑ እድምተኛች ቀድመውኝ ምዝገባ እያካሄዱ ደረስኩኝ። እኔም እንደነሱ ምዝገባዬን አከናወንኩኝና በረንዳው ላይ ቆም አልኩኝ። በአንዱ ጥግ ላይ በቅርቡ የታተመውን “የኔ ጀግና” ን ጨምሮ ሌሎች መጻሕፍትን የያዙ ወንድሞችና እህቶች አየሁና ጠጋ ብዬ የሌለኝን መርጬ ያዝኩኝ። ትንሽ እንደቆየን ወደ አዳራሽ እንድንገባ ተደረገ ቦታ ቦታችንንም ያዝን። ኤልያስም ከዲ/ን ምንዳዬ ብርሃኑ ጋር እየተመካከረ ክራሩን ለስለስ ባለ ሁናቴ የንስሃ መዝሙር ማሰማት እና ለዝግጅቱ የታደሙቱ ሁሉ እስኪደርሱ እና መርሃግብሩ አስኪጀመር ድረስ ቀድመው የመጡትን ሃሳብ ያዘ። ቀስ እያለም አዳራሹ በእድምተኞች መሞላት ጀመረ። ተጋባዥ ምሁራንና የክብር እንግዶችም የተዘጋጀላቸውን ቦታ በአስተናጋጆች አማካኝነት እንዲይዙ ተደረገ።
ልክ ፯፡፴ ሲሆን የመድረክ መሪዎቹ መሰረት ከበደ እና ዲያቆን ታደሰ ግራ እና ቀኝ ሆነው ፍፁም እትዮጵያዊ በሆነ ለዛ ለእድምተኞች ሰላምታ ካቀረቡ በኋላ በመርሃግብሩ መሰርት የመጀመሪያው የሆነው የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ማስተላለፍ መሆኑን በመግለፅ ዲ/ን ዳንኤልን ወደ መድረክ ጋበዙት እድምተኛውም በአክብሮት ተቀበለው። ዲ/ን ዳንኤል ነጨ በነጩን ግራ ቀኝ አጣፍቶ ለበሶ እንዴት አምሮበታል መሰላችሁ። ዲ/ን ዳንኤል ሰላምታ ከሰጠ እና እንኳን ደህና መጣችሁ ካለ በኋላ ፕሮግራሙን ለመታደም ተመዝግበው ከነበሩት ውስጥ ቀድመው የተመዘገቡትን ፬፻ ያህሉን እንዲሁም የተጋበዙ ፻ የሚሆኑ በአጠቃላይ ፭፻ እድምተኞች በዕለቱ እንደሚሳተፉ ተናገረ። ቀጥሎም የዝግጅቱን ዋና ዓላማ አጠር አድርጎ ገለፀ። እንዲህም አለ፤ ዋናው ዓላማ ሃሳብን ለመለዋወጥ እንዲሁም መሰል የመወያያ መድረኮችን ለማስፋት እና በጎ ስራን የሰሩ ከራሳቸው ይልቅ ለህዝባቸው ኣርአያ ለሆኑ ፭ ግለሰቦችን ዕውቅና መስጠት ነው። ከዚያም በመድረኩ የሚነሱ ሃሳቦች እና ጉዳዮች ሀገራዊ ፋይዳ እንዲኖራቸው በትህትና ጠይቆ መድረኩን ለአስተናጋጆቹ ለቀቀ።
መሰረት ከበደ ስለ ጡመራ መድረኩ እጥር ምጥን ባለ መልኩ በ፫ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከ፬፻ በላይ የተለያዩ ጽሑፎች ለአንባብያን እንደቀረቡበት፣ እነዚህም ጽሑፎች በዓለም ላይ ፻፸ በሚሆኑ ሀገራት በሚኖሩ ከ፭ ሚሊዮን በላይ እንባብያን እንደተጎበኙ ገለፀች። ቀጥላም ዲ/ን ዳንኤል በጡመራ መድረኩ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ያወጣውን ጽሑፍ በማስታወስ ይህንኑ ፅሑፍ “ይምርኃነ ያልተጠናው ስልጣኔያችን” ን ለእድምተኛው በኤሊያስ ክራር በመታጀብ አቀረበች እኛም በተመስጦ አዳመጥን። መሰረት ዲ/ን ዳንኤል ይምርኃነ እስኪደርስ የወረደውን ቁልቁለት እና የወጣውን ዳገት እኛን አስከትላ አብራው ወረደች አብራውም ወጣች። ዲ/ን ዳንኤል በዚህ ጽሑፍ ውስጥ የተለያዩ ቁምነገሮችን አስፍሯል።
የጽሑፉ ይዘት ጥንታዊውን የባህር ላይ ቤተ ክርስቲያን እና በላዩ የፈሰሰውን እፁብ ድንቅ የሆነ ጥበብ አድንቆ ለአድናቂ በመስጠት ማስደነቅ ብቻ እንዳይደለ ይሰማኛል። ታሪካችንንና ቅርሳችንን ማወቁ አንድ ነገር ነው። ይሁን እንጂ በእኔ አመለካከት ቢያንስ ቢያንስ ሁለት ዋና ዋና ቁም ነገሮችን ለማስገንዘብ ይጥራል ባይ ነኝ። የመጀመሪያው በዚያን ጊዜ እንዲህ ዓይነት ስልጣኔ ላይ የነበረ ሕዝብ ያንን የስልጣኔ ደረጃ ባለፉት የዓመታት ቁጥር መጠን ወደ ላይ ከፍ ማድረግ እንኳን ቢያቅተው ያንንው ጠብቆ ለምን አላቆየም? እንዴት የነበረውን ይጥላል? ያ ስልጣኔ ዛሬ የት ሄደ? የሚለው ሀሳብ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ይህንን የመሰለ የሀገር ኩራት የሆነ ታላቅ ሀብት በሚገባው መጠን አላጠናነውም አልተንከባከብነውምም። በተለያየ የተፈጥሮ ክስተቶች ጉዳት እየደረሰበትና ለብልሽት እየተጋለጠ ይገኛል የሚለው ሃሳብ ነው። ለዚህም ይመስለኛል ትረካውን በትኩረት የተከታተልነው። ትረካው እንዳበቃ ዲ/ን ታደሰ የሁላችንንም በተመስጦ መከታተልና ትኩረታችን ሁሉ መሰረት ላይ መሆኑን በመመልከት ዲ/ን ዳንኤል ጡመራውን በቁጭት ጀመረ በማለት የብዙዎቻችንን የውስጥ ስሜት በአንድ ዓረፍተ ነገር ገለፀው።
ቀጣዩ መርሃግብር ውይይት መሆኑን ተገልፆልን አወያዩና ለውይይቱ መነሻ ሀሳብን የሚያቀርቡ ሁለት ምሁራን ወደ መድረክ እንዲወጡ ተደረገ። አወያዩ አቶ አስራት ከበደ ናቸው። አቶ አስራትን ምናልባት ብዙዎቻችሁ ታውቋቸዋላችሁ ብዬ እገምታለሁ በተለይ በማኅበረ ቅዱሳን በሚታተሙት የሐመር መፅሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በመሆን ሲያገለግሉ የነበረ በመሆኑ። ከዚህም በተጨማሪ አቶ አስራት የተለያዩ መጻሕፍትን በግል እና ከሌሎች ጋር በመሆን እንዳሳተሙ ለምሳሌም በግላቸው የምሽት አንግዳ አንዲሁም በቅርቡ መጽሐፈ ጦቢትን ከሌሎች ጋር በመሆን ደግሞ ሚስጥሬን ላካፍላችሁ፣ ፍሬ ሊቃውንት እና ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ተጠቃሽ ናቸው። በአሁኑ ሰዓትም የአግዮስ ኅትመትና ጠቅላላ ንግድ ኃ/የተ/የግል ማኅበር ምክትል ስራ አስኪያጅ መሆናው ተገለፀልን። ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢዎቹ ደግሞ አቶ ነፃነት ተስፋዬ፣ አቶ ገዛኸኝ ፀጋው (ገዛኸኝ ፀ) እና አቶ ሊቁ ወርቁ መሆናቸው ተነግሮን ምሁራኑ ጥናራዊ ጽሁፋቸውን ማቅረብ ጀመሩ።
የመጀመሪያው አቅራቢ አቶ ነፃነት ተስፋዬ ሲሆኑ ያቀረቡትም የኢትዮጵያ ማሕበራዊ ሚዲያ አጭር ቅኝት በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነበር። በአቶ ነፃነት የቀረበው ጽሑፍ አጠቃላይ መረጃ የመስጠት ዓላማ የነበረውና ትኩረቱም በድረ ገጽ እና በፌስ ቡክ የራሳቸውን ገጽ ከፍተው የራሳቸውን ሀሳብ በሚያቀርቡት ላይ ነው። በዚህም መሰረት ስለ ብዛታቸው፣ ስለሚጠቀሙበት የቋንቋ ዓይነት፣ ስለ ይዘታቸው እና ስለሚጠቀሙባቸው የማቅረቢያ ዘዴዎች አጠር አጠር አድርገው ካቀረቡ በኋላ ለአብነትም የዲ/ን ዳንኤልን እና የፕ/ር መስፍን ወ/ማርያምን ጨምሮ የተወሰኑትን በዝርዝር አስቀምጠዋል። እነዚህ የጡመራ መድረኮች በግልም በቡድንም ስራቸውን የሚያከናውኑ ሲሆን ምን ለውጥ አመጡ በሚል ርዕስ ስር የሚከተሉትን ሃሳቦች በዝርዝር አስቀምጠዋል። የጡመራ መድረኮቹ፡-
- አማራጭ ሚዲያን መጠቀም እንደሚቻል አሳይተዋል
- አገራዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ልምድን አዳብረዋል
- ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ፣ አኮኖሚያዊ እና ሥነ-ጽሑፋዊ ሂሶችን በቀላሉ መስጠትን አስችለ
- የንባብ ባህል እንዲዳብር አስተዋጽዖ አበርክተዋል
- ልዩ ልዩ የፈጠራ ስራዎችን አበረታተዋ መድረክ ላላገኝ መድረክ ፈጥረዋ
- ሀሳብ የመስጠትና የመከራከር ባህልን አዳብረዋ ል
- ቴክኖሎጂን ለመልካም ተግባር መጠቀም እንደሚቻል አሳይተዋል
- ሕይወትን በተለያየ አቅጣጫ እንድናይ አድርገዋል
አገራዊና ዓለም አቀፋዊ መረጃዎችን በፍጥነት ማሰራጨት ችለዋል
|
ትዕግሥት ዓለም ነህ – ግጥም በፌስ ቡክ
|
አቶ ነፃነት ልክ እንደ ስማቸው ሀሳባቸውን በነፃነት ቀለል አድርገው ነው የሚያቀርቡት። ቀጥለውም ምንም እንኳን ከላይ የተዘረዘሩት ጠቀሜታዎች ቢኖሩም በብዛት የሚስተዋሉትን ችግሮች እንደሚከተለው ዘርዝረዋቸዋል። ምን ዓይነት ችግሮች ይታያሉ በሚል ርዕስ ስር፡-
- o የግል ነፃነትን መዳፈር
- o ሀሳብ ላይ ከመከራከር ይልቅ የግል ስብዕናን ማንቋሸ
- o የአንድ ፀሐፊ ሀሳብ ላይ ተቃውሞ ለምን ቀረበ በማለት አላስፈላጊ ስድቦችን መጠቀም
- o የሌላውን ሃይማኖት ማጥላላት
- o ፀያፍ ቃላትን መጠቀም
- o የቅጅ መብትን መዳፈር
- o ሀሰተኛ መረጃን ማሰራጨት
- o አስተያየት ሲሰጡ እርስ በርስ መሰዳደብ
የሚሉት በግንባር ቀደምትነት ተጠቃሾች መሆናቸውን በመግለጽ መስተካከል ስለሚገባቸው ጉዳዮች ሙያዊ አስተያየታቸውን የሚከተሉትን ሀሳቦች በማስቀመጥ ገልፀዋል።
- ጦማሪያንን ማበረታታት
- በጦማሪያን ስራዎች ላይ ተከታታይ የሆነ ሂስ መስጠት
- ጦማሪያንን ሙያዊ ስነ-ምግባርና ህግ እንዲያከብሩ ማስተማር
- የጦማሪያን ማኅበር እንዲቋቋም ድጋፍ ማድረግ
- አርአያ የሆኑትን ጦማሪያን በየ ዓመቱ እውቅና መስጠት (መሸለም)
- በጡመራ መድረኮች ላይ የሚወጡ የተመረጡ ጽሑፎችን በጋራ ማሳተም
- በጦማሪያን ጽሑፎች ላይ በከፍተኛ ት/ት ባለሙያዎች ጥናት ማድረግ
አቶ ነፃነት ጊዜ ገድቧቸው የውይይት መነሻ ሃሳባቸውን በዚሁ አጠናቀቁ። ሁለተኛው አቅራቢ አቶ ገዛኸኝ ፀጋው ናቸው እርሳቸውም “በዲ/ን ዳንኤል ጽሑፎች ላይ ሙያዊ ዳሰሳ” በሚል ርዕስ ዳሰሳቸውን ጀመሩ። አቶ ገዛኸኝ ፀ በዳሰሳቸው ወቅት በቅድሚያ ያነሱት ጉዳይ የአንደኛ ዓመቱ ሲከበር ተሰጥው የነበሩ አስተያየቶችና ሂሶች በቀጣዮቸቹ ጽሑፎች ላይ እንዴት ተተገበሩ ምንዓይነት ለውጦችስ ታዩ በማለት እይታቸውን አቀረቡ። አቶ ገዛኸኝ ፀ በውይይት ወቅት አንድ ለየት የሚያደግ ፀባይ አላቸው። የመጀመሪያው ንግግራቸውን በተለያዩ ነገሮች ስለሚያዋዙት ለአድማጭ አይሰለችም። ሁለተኛው ደግሞ ዕውቀት በስሜት ሊታጀብ ይገባዋል የሚል አቋም አላቸው። በንግግራቸው ወቅት አብዛኛው የሰውነት ክፍላቸው ይንቀሳቀሳል በተለይ እጃቸው። የንግግር ጊዜያቸው በጨመረ ቁጥር እያንዳንዱ ባህሪያቸው አብሮ ይጨምራል፤ ድምፃቸው፣ ፍጥነታቸው፣ የእጃቸው እንቅስቃሴ … በቃ ምን አለፋችሁ ሁሉም ይጨምራል። ቢሆንም ግን ውበት አለው። እኔ ግን ንግድ ሚንስቴር እንዳያያቸው አልኩኝ (በውስጤ)።
አቶ ገዛኸኝ ቀጥለውም በዲ/ን ዳንኤል የጡመራ መድረክ ላይ የሚቀርቡ ጽሑፎች በይነ ዲስፕሊናዊ ይዘትን የተላበሱ ናቸው በማለት ገለጿቸው። እነዚህ ጽሑፎችም ሀገርኛ በሆነ የአቀራረብ ለዛ እና ስልት የተቃኙ ሲሆኑ አንዳንዶቹም በዲ/ን ዳንኤል ሀሳቦችን ገልብጦ የማስቀመጥ (paradox) ብቃት የአንባቢን ትኩረት የመሳብ አቅም ያላቸው ናቸው በማለት አክለውበታል። አቶ ገዛኸኝ ፀ በጡመራ መድረኩ ላይ የወጡትን ጽሑፎች በተለይም በ”የኔ ጀግና” መጽሐፍ ውስጥ የታተሙት ላይ ትኩረት በማድረግ አብዛኞቹን ጽሑፎች በወግና በመጣትፎች ስር በመፈረጅ ጽሑፎቹ የአስተሳሰብ አምድ ለውጥ የላቸውም ሲሉ ሞግተዋል።
የቆመለት ሀሳብ ላይ መደጋገም ይታያል ይህም ደግም የዲ/ን ዳንኤል የማንነቱ መገለጫ በመሆኑ የሚጠበቅ እና ጤናማ አካሔድ መሆኑን በመግለፅጽ የተለያዩ ጽሑፎችን እንደ አብነት ለማሳያነት አቅርበዋል። የጭብጥ መመሳሰል ላሉት የገና ስጦታነ፣ ሻካራ እጆችን እና የኔ ጀግናን እንደ አብነት ሲያነሱ የቅርጽ አቀራረብ መመሳሰል ላሉትም ማኅሌትና መክፈልት፣ ብርሌ እና ያሳዘነኝ ባንተ መመስገኔን ሲያቀርቡ የተለያዩ የአቀራረብ ዘዴ የተከተሉ ላሏቸው ደግሞ ከንቲባ ሆኛለሁ እና ስኳሬና ዘይቴ የሚሉትን አንስተዋል። አቶ ገዛኸኝ ሲያጠቃልሉም የዲ/ን ዳንኤልን ጽሑፎች ለብዙዎች ተደራሽ መሆን ዋናው ምክንያት ጽሑፎቹ ጽንፈኛ አቋምን ስለማያንፀባርቁ ነው በማለት የጽሑፎቹን ይዘት ጥቁርም አይደሉም ነጭም አየደሉም ይልቁንም ግራጫ ናቸው ብለዋቸዋል።
|
ገዛኽኝ – ትንተና
|
በመጨረሻም በያዘው ጭብጥ እጅግ የተሳካለት እና የሀሳብና የሀብት ልዩነት የሚፈጥሩትን የባይተዋርነት ስሜት አጉልቶ አሳይቷል ያሉትን “ዶሮና የሁለት ልጆች ፈተና” ጽሑፍ የመጨረሻውን አንቀፅ ”አየህ የሀብታሞችና የድኾች ሃይማኖት እዚህ ሀገር ይለያያል፡፡ ሀብታሞች መብልን እኛ ደግሞ ጦምን እናበዛለን፡፡ እነርሱ በደም ብዛት እኛ በደም ማነስ እንታመማለን፣ እነርሱ በስኳር ብዛት እኛ በስኳር እጥረት እንቸገራለን፣ እነርሱን ውፍረት እኛን ክሳት ያስቸግረናል፡፡ የነርሱ ልጆች አልበላም ብለው የኛ ልጆች እንብላ ብለው ይገረፋሉ፡፡ እነርሱ ገብርኤልን እኛ ሚካኤልን እንዘክራለን፡፡ በዚህ ምክንያት ሃይማኖታችን ተለያይቷል፡፡” የሚለውን ለታዳሚው በማንበብ ይህ ጽሑፍ “የኔ ጀግና” በሚለው መጽሐፍ ውስጥ ሊካተት ይገባው ነበር በማለት የግል አስተያየታቸውን በመስጠት ሃሳባቸውን ቋጭተዋል።
፫ኛው ጽሑፍ አቅራቢ ባጋጠማቸው የፕሮግራም መጣበብ ምክንያት መምጣት አለመቻላቸውንና በዚሁም ምክንያት አዘጋጆቹንና የዝግጅቱ ታዳሚዎችን ይቅርታ መጠየቃቸው በአወያዩ በኩል ተነገርና ወደ ቀጣዩ መርሃግብር አመራን። ይህ መርሃ ግብር ሌሎች ጦማሪያን ልምዳቸውን ለታዳሚዎች የሚያቀርቡበት ነው። ልምዳቸውን እንዲያካፍሉ የተጋበዙትም ተራ በተራ ወደ መድረክ እየወጡ ለመጦመር ምን እንዳነሳሳቸው እና በጡመራው ሂደት ውስጥ ስላጋጠሟችው በጎ እና ተስፋ አስቆራጭ አጋጣሚዎች እያዋዙ አጫወቱን። እነዚህ ጦማሪያን ህይወት (የነቆራና ሌሎችም ጦማሪት)፣ ዘሪሁን (የተለያዩ ሀሳቦችን በራሱ ብሎግ የሚያቀርብ) እና ትዕግስት (ግጥሞችን በፌስቡክ የምታቀርብ) ናቸው።
በቀጣይነት የቀረበው ደግሞ ጸሐፊያን ለሚጽፏቸው እና ወደ አንባቢያን ለሚልኳቸው ጽሑፎች ምን ያህል ሊጠነቀቁ እና ኃላፊነት ሊሰማቸው እንደሚገባ ያመላከተ የፊልም ግብዣ ነበር። ዲ/ን ዳንኤል “እኛ የመጨረሻዎቹ” በሚል ርዕስ የጻፈውን ጽሑፍ የአንድ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ድራማዊ በሆነ አቀራረብ እየተቀባበሉ ደስ በሚያሰኝ የሕፃንነት የድምጽ ቅላፄ በት/ት ቤቱ ለነበሩ ታዳሚያን ያቀረቡት ነበር። ሕፃናቱን ያሳድጋችሁ ብለን መረቅንና በጉጉት ወደሚጠበቀው ዕውቅና የመስጠት መርሃ ግብር አመራን።
ይህ መርሃግብር በጎ ላሰቡ አና ላደረጉ፣ ከራሳቸው ይልቅ ለሌሎች እንዲሁም ለሃገር ጠቃሚ የሆነ ተግባር ላከናወኑና መልካምነታቸው ለሌሎች አርኣያ ሊሆን የሚችሉ ሰዎችን እውቅና የሚሰጥበት ዝግጅት ነው። ለዚህም ተግባር ለ፩ ወር ያህል የቆየ የጥቆማ ጊዜ መሰጠቱ ይታወሳል። ይህንን ዝግጅት በተመለከተ አስተባባሪው ወደ መድረክ ወጥተው እንዳንድ ገለፃዎችን አደረጉ። የዝግጅቱን ዓላማ እንደሚከተለው አጠር አድርገው ገለፁት።
- እንዲህ ያለውን ተግባር እንደ ባህል እንዲጎለብት ለማድረግ፣
- ለፈፀሙት በጎ ተግባር ለማመስገን እና
- ቁጥራቸውን ለማብዛት
መሆኑን በመግለጽ በ፻፶፱ ጠቋሚዎች አማካኝነት ፸ ግለሰቦችና ፮ ተቋማት እንደተጠቆሙ ከዚያም ፯ አባላት ያሉት የዳኞች ኮሚቴ መቋቋሙን ኮሚቴውም መስፈርቶችን በማዘጋጀት በመጀመሪያ ማጣሪያ ከ፸፮ቱ ተጠቋሚዎች ፲፯ቱን እንደመረጠ እና ከእነዚህም ውስጥ የመጨረሻ ማጣሪያ በማድረግ ፭ቱ የዓመቱ በጎ ሰዎች መመረጣቸውን ለታዳሚው አብራሩ። ቀሪዎቹም ፲፪ በጎ ሰዎች ያደረጉት በጎነት ወደፊት በጡመራ መድረኩ ላይ እንደሚወጣ ተገለፀና ለ፭ቱ ግለሰቦች ዕውቅና ወደ መስጠቱ ተገባ።
እነዚህ ፭ ሰዎች (ከ፩ እስከ ፭ የተባለው ለአፃፃፍ እንዲያመች እንጂ መበላለጥን አያሳይም)
፩ኛ ንቡረ እድ ገብረ ህይወት መልሴ
፪ኛ አቶ ቢንያም በለጠ
፫ኛ ወ/ሮ መዓዛ ብሩ
፬ኛ ደራሲ እንዳለጌታ ከበደ
፭ኛ ዶ/ር እሌ ገ/መድህን
ሲሆኑ የተዘጋጀላቸውን የምስክር ወረቀት ከመጋቢ ሚስጥር አባ ቴዎድሮስ አካሉ እና ከ ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን እጅ ተቀብለዋል። ፭ቱ የዓመቱ በጎ ሰዎች ምን ሰርተው ተመረጡ? ለማወቅም ሆነ አርአያነታቸውን ለመከተል በሚያስችል መልኩ የእያንዳንዳቸው ጥረት እና ሰኬት በዝርዝር በዲ/ን ዳንኤል ሊቀርብ እንደሚችል በማመን ወደሚቀጥለው ልለፍ። ቀጥሎም በመድረክ ላይ ከሚካሔዱት መርሃ ግብሮች መካከል የመጨረሻ የሆነው የውይይት ክፍለ ጊዜ ተካሔደ። በውይይቱም ወቅት ለሁለቱ ጽሑፉ አቅራቢዎችና ለዲ/ን ዳንኤል የየተለያዩ ጥያቄዎችና አስያየቶች በታዳሚዎች ተሰጥተዋል። ምላሽ ለሚያስፈልጋቸው ተገቢው መልስ የተሰጠ ሲሆን ሌሎቹን በአስተያየት መልክ ተወስደዋል።
ከዚያም ዲ/ን ዳንኤል ይህ መሰሉ በዓል በየ ሁለት ዓመቱ ዕውቅና መስጠቱ ግን በየዓመቱ እንደሚካሔድ በመገለፅ፣ ለዝግጅቱ መሳካት የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉትን ሐኮማልን እና አግዮስን፣ ይንን ፕሮገራም በተሳካ ሁኔታ እውን እንዲሆን ለደከሙት አዘጋጆች እና ጥሪው አክብረን ለመጣነው ታዳሚዎች ልባዊ ምስጋናውን አቀረበ። ቀጥሎም መሰረት ከበደ የፕሮግራሙን መጨረሻ ተናገረች ይኸውም በዝግጅት ኮሚቴው አማካኝነት ለዲ/ን ዳንኤል የተዘጋጀውን ሽልማት በአቶ ነፃነት ተስፋዬ አማካኝነት መስጠት መሆኑን ገልፃ በተግባርም ተደረገ። ሽልማቱም የታላቁን ሐዋርያ የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን ምክር የያዘ ፎቶ ነወ። በፎቶው ጎን ካለው ጽሑፍ ውስጥ የመጀመሪያውን ዓረፍተ ነገር ዲ/ን ዳንኤል አነበበልን አኛም የአባታችን ቡራኬ ይድረሰን አልን። ከታዳሚው መካከልም አንዲት እናት ዲ/ን ዳንኤልን ለዚህ እንዲበቃ ከጎኑ ሳትለይ ለረዳችው ለባለቤቱ ለጽላት የራሳቸውን ሽልማት በዲ/ን ዳንኤል በኩል አበረከቱ። ዲ/ን ታደሰ ደግሞ የመጨረሻውን መጨረሻ ተናግሮ ፕሮግራሙ ልክ ፲፪ ሰዓት ላይ ተጠናቀቀ።
|
ሻሂ ቡና
|
በመጨረሻም ትህትናን በተላበሱ የአክሱም ሆቴል ሰራተኞች አማካኝነት ሻይ ቡና ተጋብዘን ከዲ/ን ዳንኤል ጋርም የማሰታወሻ ፎቶ ተነስተን እንዲሁም በያዝኩት መጽሐፍ ላይ ዲ/ን ዳንኤልን አስፈርሜ ለዚህ ስኬቱ ጀነሬተሩ የሆነችውን ጽሉንም ከእርሱ ፊረማ ጎን አስፈርሜ ተለያየን። ከዚያም ጉዞ ወደ አራት ኪሎ ሆነ። እንግዲህ የዳንኤል ክብረት እይታዎች የ፫ኛ ዓመቱ በዓል ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስል ነበር።
ሰላም ሁኑ