የ500 ዓመቱ ዛፍ


ወደ እንጭኒ መንገድ- ልብ የሚመስጥ የፈረስ ሜዳ

አሁን በምዕራብ በኩል በቡራዩ በር እየወጣን ነው፡፡ ሆሎታ አንድ ሰዓት ላይ ስንደርስ ከእኛ ጋር ለጉዞ የተዘጋጀውን የሆሎታ ኒያላ ሆቴል ባለቤት ያሬድን በእግር በፈረስ መፈለግ ጀመርን፡፡ ሆቴሉም አልገባም፣ በቤቱም የለም፡፡ በግቢው በር ላይ ያገኘነው ሰውም የት እንደሄደ መንገር አልፈለገም፡፡ ዘመድ አይጥፋ አፈላልገን አድራሻውን አገኘነው፡፡ ለካስ የሌሊት መርዶ ገጥሞት ሄዶ ነው፡፡
ያዘጋጀው መኪና የቤት መኪና ነው፡፡ ‹መንገዱ ቀና ስለሆነ ይህም ሊገባ ይችላል› የሚል መረጃ አግኝቷል፡፡ እኛም ይሁን ብለን መኪና ውስጥ ገባንና ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት አካባቢ ከሆሎታ ወደ እንጭኒ ጉዞ ጀመርን፡፡ መንገዱ የተወለወለ አስፓልት ነው፡፡ እንደ አንዳንድ የመውጫ መንገዶችም ዘሎ ጥልቅ የሚል ሀገርኛ ሰውና ከብት የለም፡፡ እኔ፣ ከጀርመን የመጣው ሻምበል(ቀሲስ አብርሃም በለጠ) እና ያሬድ የሀገራችንን ወግ እያወጋን በመኪና ተወዘወዝነው፡፡
ሀገሩ የፈረስ ሀገር ነውና ሰላሌን የሚያስንቅ ሜዳ አለው፡፡ ዓይን ይታክታል እንጂ ሜዳው አያልቅም፡፡ ፈረሶቹ ደግሞ ከአንበሳና ከቀጭኔ የተዋለዱ ነው የሚመስሉት፡፡ ቁመታቸው እንደ ቀጭኔ ስፋታቸው እንደ ዳልጋ አንበሳ ነው፡፡ ጋማቸው ለ‹ሚስ› ምናምን የሚወዳደሩትን ፀጉር ያስንቃል፡፡ 

ከአንድ ሰዓት ጉዞ በኋላ እንጭኒ ደረስን፡፡ ያሬድ ከመኪና ወረደና የሚያውቃቸውን ሰዎች ስለ መንገዱ ጠየቃቸው፡፡ ‹የወለንኮሚ መንገድ እየታረሰ ነው፡፡ ገጠሮችን ከዋና ዋና መንገዶች ጋር ለማገናኘት በተያዘው ሀገር ዐቀፍ ዕቅድ መሠረት ወለንኮሚን ከእንጭኒው ዋና መንገድ ጋር ለማገናኘት የመንገድ ሥራ እየተሠራ ነው፡፡ መንገዱ በግሪደር ታርሷል፡፡ አሁን እንኳን የቤት መኪና ትልቁም በምጥ ነው የሚገባው› አሉን፡፡

ታድያ ምን እናድርግ? ወደ ወለንኮሚ የሚሄዱ መኪኖችን ማፈላለግ ጀመርን፡፡ እንደሰማነው ወደ ወለንኮሚ ለመሄድ አማራጩ ሦስት ነው፡፡ የመጀመርያው በጭነት መኪኖች መሄድ ነው፤ ሁለተኛው ለመንገድ ሥራ የሚንቀሳቀሱ መኪኖችን መለመን፤ ሦስተኛው ደግሞ በመደበኛነት የሚሠሩትን ሁለቱን ሎንቺኖች መጠበቅ፡፡ 

ወደ ሙገር በረሃ ስንወርድ

የጭነት መኪናውን ለማግኘት አልቻልንም፡፡ እዚያው እንጭኒ ሆነን ሁለት ሰዓት ፈጀን፡፡ ለመንገድ ሥራው የሚገቡ መኪኖችም ለመተባበር አልቻሉም፡፡ የነበረን አማራጭ ሁለቱን ሎንቺኖች መጠበቅ ነው፡፡ ሎንቺኖቹ የሚቆሙት ከከተማው ገባ ብለው መንደር ውስጥ ነው፡፡ አንዱ ወለንኮሚ ሌላው እንጭኒ ይቆሙና ሲሞላላቸው ይነሣሉ፡፡ የመጣንባትን መኪና በአካባቢው ሰዎች ዘንድ ‹ዶክተር› እየተባሉ በሚጠሩ አንድ የሕክምና ባለሞያ ግቢ አቆምንና ሎንቺኖቹን ፍለጋ ወደ መንደሩ ዘለቅን፡፡
እውነትም አንዲት ሎንቺና ቆማለች፡፡ በነገራችን ላይ ሎንቺና የጣልያን ስም ነው፡፡ መጀመርያ ወደ ሀገራችን ከገቡ መኪኖች ከነ ትሬንታ ኳትሮ፣ ሴንቼንቶ ጋር አገር ያቀኑ ናቸው ሎንቺናዎች፡፡ አሁን አሁን ዘመናዊ አውቶቡሶች ሲመጡና ውድድሩን መቋቋም ሲያቅታቸው ሎንቺኖች ከተማውን ለቅቀው ወጡ፡፡ ገጠሩንና ግብርናውን ማዕከል አድርገውም ገጠር ገቡ፡፡ እዚያ የተሰበረ ዕቃቸውን በገመድ እያሠሩም ቢሆን ሕዝብ ያገለግላሉ፡፡

ወደ ሙገር በረሃ ስንወርድ

ወደ ሎንቺናው ስንገባ የተወሰኑ ሰዎች ተኝተዋል፤ የተወሰኑት ደግሞ ለቦታ መጠበቂያ ዕቃቸውን አኑረው ወርደዋል፡፡ ሾፌሩ ግን የለም፡፡ በአካባቢው ያገኘናቸውን ልጆች ስንጠይቃቸው ሾፌሩ ‹ሲሞላ ጥሩኝ› ብሎ መሄዱን ነገሩን፡፡ እኛም ይሞላ ዘንድ ልንጠራው ሄድን፡፡ ሾፌሩ ያገኘውን ይዞ በጎደለው እኛ ሞልተን ልንሄድ ተስማማንና ከቤቱ ወጣ፡፡ ሞተሩን ማንቀሳቀስ ሲጀምር ተሳፋሪው ሁሉ ከየቤቱ ወጣና መኪናውን ሞላው፡፡ እኛም ብዙ ከመክፈል የዳንን ስለመሰለን እፎይ አልን፡፡ ከሰዓት በኋላ ሰባት ሰዓት አካባቢ በሎንቺን ከእንጭኒ ወደ ወለንኮሚ ጉዞ ጀመርን፡፡ መንገዱ ተጠርጎ አፈር ባፈር ሆኗል፡፡ መኪናው ይስበናል፣ ይመልሰናል፣ ያነሣናል፣ ይጥለናል፡፡ ወተት ብንጠጣ ኖሮ ቅቤ ይወጣን ነበር፡፡
ለሁለት ሰዓት ያህል ከተጓዝን በኋላ ወለንኮሚ ገባን፡፡ አሁን ወደ ቆላው የሚወስደን ሰው ያስፈልጋል፡፡ የምንጓዘው ከ500 ዓመታ በፊት ወደተተከለው ወደ ደብረ ጽሙና ገዳም ነው፡፡ ገዳሙን የመሠረቱት አቡነ ተክለ ሐዋርያት ናቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሐዋርያት በሙገር አካባቢ የተወለዱ፣ በደብረ ሊባኖስ ያገለገሉ፣ በጎንደርና በትግራይ፣ በይፋትና በዝዋይ ያስተማሩ አባት ናቸው፡፡ ግፍና መከራን የማይታገሡ፣ የሰው መብት ሲነካ የማይወዱ፣ ከአጥቂው ርቀው ከተጠቂው ጋር የሚቆሙ አባት ናቸው፡፡
ለብዙ ዘመን ካስተማሩ በኋላ የንጉሥ ዘርዐ ያዕቆብ ባለቤት እቴጌ ዣን ከለላ በእሥር ቤት ሆና ልካባቸው ነበር፡፡ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ከአምልኮ ባዕድ ጋር በተያያዘ ብዙ ሰዎችን አሥሮ፣ በሞት እንዲቀጡም አድርጎ ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ፖለቲካዊና ጥቅማዊ የሆነውን ነገር ወደዚህ ጉዳይ በማጠጋጋት የተፈረደባቸው ነበሩ፡፡ በዚህ ሁኔታ ከታሠሩት መካከል እቴጌ ዣን ከለላና ንጉሥ በዕደ ማርያም ይገኙበታል፡፡

የሙገር በረሃ

እቴጌ ዣን ከለላ ያደረገችላቸውን ጥሪ ተቀብለው የንጉሡን ትእዛዝና ዐዋጅ ሳይፈሩ ተክለ ሐዋርያት መጡ፡፡ እቴጌይቱና ልጃቸው የታሠሩበት አደገኛው እሥር ቤትም ውስጥ ገብተው አናገሯቸው፣ አስተማሯቸው፣ አጽናኗቸውም፡፡ ከዚያ እሥር ቤት ሲወጡም ባመኑ ሰዎች ዘንድ ሊደረግ የማይገባው ነገር በንጉሡ አደባባይ በደብረ ብርሃን ሲደረግ አዩ፡፡ በመስቀል በዓል ዕለት የፈረስ ጉግስ ጨዋታ ሲደረግ ወታደሮቹ በሕዝቡ ላይ ይጫወቱ ነበር፡፡ በዚህ ጨዋታ ምክያትም ብዙ ሰው ይገደል ነበር፡፡ እንዲያውም አንዳንድ አፈ ታሪኮች ወታደሮቹ ጠግበው የሰውን ጭንቅላት እንደ ዕሩር ይጫወቱበት ነበር ይላሉ፡፡
 ሜዳው በሰው አጥንት ተመልቶ ያዩት ተክለ ሐዋርያት ይህ በሰው ልጅ ላይ ሥልጣንን ተገን አድርጎ የሚሠራው ግፍ ዕረፍት ነሣቸው፡፡ በአካባቢው የነበሩትን ታላላቅ ሰዎች ይህ ግፍ ሲሠራ ለምን ዝም እንደሚሉ ሲጠይቋቸው ‹ንጉሡን እንፈራዋለን› የሚል መልስ ሰጧቸው፡፡ ‹እንጀራችንን እናጣለን› ማለታቸው ነው፡፡
ተክለ ሐዋርያት ንጉሡን ለማናገር ቀጠሮ ጠየቁ፡፡ ነገር ግን ንጉሡ እርሱ ስላልተመቸው ለአንድ ባለሟሉ ሃሳባቸውን እንዲነግሩት ላከው፡፡ ተክለ ሐዋርያት ሳይፈሩና ሳያፍሩ እየተሠራ ያለውን ግፍ፣ ይህ ግፍ እየተደረገ አድራጊውም ሕዝብ፣ ፈቃጁም ንጉሥ ክርስቲያን መባል እንደማይገባቸው፤ ያለ ፍርድ እንዲሁ ሰዎች እየታሠሩ እንደሚሰቃዩ፤ ይህንን የጭካኔና የፍርደ ገምድልነት ሥራ እንዲያስቆም ለዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ እንዲነግረው ለመልክተኛው ላኩበት፡፡ 

ንግሥት ዘውዲቱ ያሠሩት የጥንቱ የደብረ ጽሞና ቤተ ክርስቲያን

ንጉሥ ዘርዐ ያዕቆብ ይህንን ሲሰማ ተቆጣ፡፡ አቡነ ተክለ ሐዋርያትንም ጠርቶ የተናገሩት እውነት መሆኑን ጠየቃቸው፡፡ ተክለ ሐዋርያትም እየተሠራ ያለውን ግፍና ፍርደ ገምድልነት በጥብዐት በንጉሡ ፊት ነገሩት፡፡ ከዚያ በኋላ የመከራ መዓት አዘነበባቸው፡፡ አጥንታቸው እስኪታይ ተገረፉ፤ የጨለማ እሥር ቤት ተወረወሩ፤ በየቀኑ በሽመል እንዲገረፉ ተደረገ፤ ዓባይ በረሃ ጉድጓድ ውስጥ ለሰባት ወራት ያህል እግርና እጅ በሚቆነጥጥ ብረት ታሠሩ፤ በመጨረሻም እየተደበደቡ በጨለማ እሥር ቤት ውስጥ ሞቱ፡፡ በአካባቢውም በአባ በርሶማ ገዳም በድብቅ ተቀበሩ፡፡

በመፍረስ ላይ የሚገኘው የጥንቱ ቤተ ክርስቲያን

ካረፉ ከ13 ዓመት በኋላ ንጉሥ በዕደ ማርያም በነገሠበት ዓመት በ1468 ከተጉለት ወደ ምዕራብ ሸዋ ሙገር በረሃ ደብረ ገብርማ ዐጽማቸው በክብር ተመለሰ፡፡ አሁን እየሄድን ያለነው ወደዚህ ቦታ ነው፡፡ 
ከሎንቺናዋ ወርደን ዘወር ዘወር ስንል አንዲት አብረውን የመጡ እማሆይ አየን፡፡ ስንከተላቸው ‹ገዳም ሻሂ ቤት› ወደሚል ቤት ገቡ፤ እኛም ጠጋ አልን፡፡ ‹ወደ ገዳም ይወርዳሉ?› አልንና ጠየቅናቸው፡፡ ‹አዎን እወርዳለሁ ግቡ› አሉን፤ ወደማናውቀው ቤት ተከትለናቸው ገባን፡፡ እንጀራና ጠላ ቀረበልን፡፡ ወይ ሀገር ኢትዮጵያ የማታውቁት ሀገር፣ የማታውቁት ቤት ገብታችሁ ስማችሁን እንኳን ያልጠየቋችሁ ሰዎች ምግብና መጠጥ ያቀርቡላችኋል፡፡ ማነህ? ከየት ነህ? የማን ወገን ነህ? የጠየቀን አልነበረም፡፡
ጥቂት ቆይተን ወግ ተጀመረ፡፡ የሚገርመው ነገር ያስተናገዱን ሰዎች የሻምበል ዘመድ ሆነው ተገኙ፡፡ ከዚያማ የሞቀው መስተንግዶ እንደገና ደራ፡፡ ቡና ጠጣንና ከእማሆይ ጋር ወደ ቆላው ለመውረድ ተነሣን፡፡ በታረሰው መንገድ በኩል ከተማዋን ለቅቀን ለአርባ አምስት ደቂቃ ያህል ወደ ቆላው ተጓዝን፡፡ ቁልቁለት ስለሆነ ብዙም አልተቸገርንም፡፡ 

አዲሱ የደብረ ጽሞና ቤተ ክርስቲያን

ደብረ ጽሙናን ከፊታችን አገኘነው፡፡ ገዳሙ ሁለት ቦታ ላይ ነው፡፡ የጥንቱ ገዳም ‹ደብረ ገብርማ› ይባላል ሙገር በረሃው ውስጥ ነው፡፡ ወደ እርሱ ለመሄድ ከዚህ በኋላ ቢያንስ የአንድ ሰዓት ተኩል መንገድ መጓዝ ይጠይቃል፡፡ ሁለተኛው ከተራራው ወገብ ላይ በሚገኝ ረባዳ ሥፍራ ላይ ይገኛል፡፡ ይህኛው የተተከለው በንግሥት ዘውዲቱ ጊዜ በ1907 ዓም ነው፡፡ በውስጡ ሁለት አብያተ ክርስቲያናት አሉት፡፡ አንደኛው አሁን መቶ ዓመት ሊሞላው  ሁለት ፈሪ የቀረውና እየተሰነጣጠቀ ልፍረስ ልፍረስ የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከጥቂት ዓመታት በፊት አዲስ አበባ በሚገኙ ወጣቶች ትብብር የተሠራው ማራኪ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ እዚህ የሚዘል ጉሬዛ፣ የሚያዜሙ ወፎች፣ የሚዘምሩ የአብነት ተማሪዎችና በሹክሹክታ ከዛፎቹ ጋር የሚያወራ ነፋስ ብቻ ይገኛል፡፡ 

በገዳሙ የእንግዳ ማረፊያ

እኛም አዳራችንን በእማሆይ ቤት አደረግን፡፡ እግር አጥበው፣ ወጥ ቀቅለው፣ ዳቤ አምጥተው ነበር የተቀበሉን፡፡ እርሳቸው ዘንድ ልዩ ሻሂ አለ፡፡ ያለ ሻሂ ቅጠል የሚሠራ፣ ያውም ‹ካፊን› የሌለበት፡፡ ሳምንት አወጋችኋለሁ፡፡ 

አብርሃማዊ የእንግዳ አቀባበል