ጉዱ ካሳ እና “ሰበነክ-ሊቃውንት”
ኤፍሬም እሸቴ
እንግሊዛዊ ሆኖ “ሼኪስፒርን የማያውቅ፣ ሥራዎቹንም ያላነበበ፣ ኢትዮጵያዊ ሆኖ ሀዲስ ዓለማየሁን የማያውቅ ‘ፍቅር እስከ መቃብርን’ም ያላነበበ” ቢኖር እጅግ የሚደንቅ ይሆናል። እንዲያውም ጥያቄው ‘ስንት ጊዜ አነበብከው?’ እንጂ ‘አንብበኸዋል እንዴ?’ አይሆንም የሚል ግምት ነበረኝ። ከዕለታት በአንዱ ቀን በድሮ የትምህርት ቤት መጽሐፎቻችን ውስጥ ስላሉ ታሪካዊ ጽሑፎች ስናወጋ በመካከሉ አብዲሳ አጋን አስታወስን። “ስንተኛ ክፍል መጽሐፍ ውስጥ ነበር ጃል?” እያልን ስንጠያየቅ አጠገባችን የነበረ አዕምሮው ብሩህ የሆነ ልጅ እግር የዩኒቨርሲቲ መምህር “ማነው አብዲሳ አጋ?” የሚል ጥያቄ አቀረበ። በመጀመሪያ እንደ ቀልድም ወሰድነው። ቀጥሎ እንደ መገረምም አደረገን።