ወርቁ ሰው
ሰሞኑን የአሜሪካኖችን የተረት መጽሐፍ ሳነብ እንዲህ የሚል ታሪክ አገኘሁ፡፡ እኔ በአበሻኛ ላውጋችሁ፡፡
ሰውዬው ሁሉን ለኔ ብቻ የሚል ዓይነት አይጠግቤ ሰው ነው አሉ፡፡ ያየውን መልካም ነገር ሁሉ የርሱ ማድረግ አልነበረም ዓላማው የርሱ ብቻ ማድረግ እንጂ፡፡ የሚደሰተውም እርሱ ሲኖረው ሳይሆን እርሱ ብቻ ሲኖረው ነው፡፡ እርሱ ብቻ እንዳለው ያሰበውን ነገር ሌሎችም ሰዎች እንዳላቸው ሲሰማ ያዝናል፡፡ አንዳንዴ በዓለም ላይ እርሱ ብቻ ኖሮ ይህ የሚያየው ሀብት፣ ሥልጣንና ገንዘብ ሁሉ የራሱ ብቻ እንዲሆን ይመኛል፡፡
አንድ ቀን እርሱ ብቻ ሊያገኘውና ከሰዎች ሁሉ ሊበልጥበት የሚችለውን ነገር ሲያስብ ቆየ፡፡ በመጨረሻም «ምናለ የምነካው ነገር ሁሉ ወርቅ በሆነልኝና እኔ ብቻ በዓለም ላይ ወርቅ በወርቅ በሆንኩ» ብሎ አሰበ፡፡ ይህንን ሃሳቡን ለመፈጸምም እልም ያለ በረሃ ውስጥ በሚገኝ ዋሻ ወደሚኖር ጠቢብ ዘንድ ሄደ፡፡ ከብዙ ድካምና ፍለጋ በኋላም ያንን ጠቢብ አገኘውና ሃሳቡን አጫወተው፡፡
ጠቢቡ ሰው ለጥቂት ጊዜ በጉዳዩ ላይ አሰበበትና «ወዳጄ ሃሳብህ በርግጥም በዓለም ላይ የናጠጥክ ብቸኛ ሀብታም የሚያደርግህ ነው፡፡ ነገር ግን አይጠቅምህምና ይቅርብህ» አለው፡፡ ያም ሰው «ለምን? ብቸኛ ሀብታም የሚያደርገኝ ከሆነ ለምን አይጠቅመኝም? ሲል ጠየቀው፡፡ «አየህ አንድን ነገር ለብቻ መያዝ የሚያስደስት ይመስልሃል እንጂ አያስደስትም፡፡ ያኔ ዛሬ እንደምታስበው አትሆንም፡፡ አንድን ነገር ለብቻ መያዝ ያሰለቻል፡፡ ያቅለሸልሻል፡፡ ከተወሰነ ጊዜ በኋላም ትርጉም ታጣበታለህ፡፡ ማካፈል የሌለው ሕይወት ደስታ አይኖረውም፡፡» አለው፡፡
ሰውዬው ግን እጅግ ዘበዘበው፡፡ ያን ጊዜም ጠቢቡ «ምንም ችግር የለውም እኔ የምትፈልገውን ነገር አደርግልሃለሁ፤ ችግሩ ግን መመለስ አትችልም፡፡ የምትመለሰው ሞተህ ብቻ ነው» አለው፡፡ ሰውዬውም «እስክሞት ድረስ ብቸኛ ሀብታም ከሆንኩ ምን ችግር አለ» አለና ሳቀ፡፡
ጠቢቡ «ይህንን መድኃኒት ሰውነትህን እቀባልሃለሁ፤ የነካህውም ሁሉ ወርቅ ይሆንልሃል፡፡ ያንን ማድረግ የምትችለው አንተ ብቻ ነህ፡፡ እኔ ግን የዚህ መድኃኒት ማርከሻ የለኝምና መመለስ ብትፈልግ አልረዳህም» አለው፡፡ ሰውዬው እጅግ ተደሰተ፡፡ ታየው፤ የሚነካው ነገር ሁሉ ወርቅ ሲሆንና በወርቅ ላይ ተቀምጦ በወርቅ ላይ ሲተኛ፤ በወርቅ ላይ በልቶ በወርቅ ላይ ሲጠጣ፤ ወርቅ ለብሶ ወርቅ ሲጫማ፤ በወርቅ ላይ ተራምደ በወርቅ ላይ ሲንሳፈፍ፡፡ ታየው፡፡
ግን ደግሞ ገረመው፡፡
«ይህንን ጥበብ እያወቅክ ግን ለምን አንተ አልተጠቀምክበትም?» አለና ጠቢቡን ጠየቀው፡፡
«ቅድምኮ ነገርኩህ፡፡ ሀብትም፣ ሥልጣንም፣ ክብርም፣ ዝናም፣ ውበትም የሚያስደስተው ሲካፈሉት ብቻ ነው፡፡ ብቻውን ሀብታም፣ ብቻውን ንጉሥ፣ ብቻውን ቆንጆ፣ ብቻውን ክቡር፣ ብቻውንም ዝነኛ የሆነ ሰው የሚቀርበውና የሚያጫውተው፣ የልቡን የሚያወራውና እኩል አብሮት የሚቆም አያገኝም፡፡ ልክ አንድ በጣም ረዥም ሰው በድንኮች ተከብቦ ቢቆም ምን ይሰማዋል፡፡ በድኾች ብቻ የሚከበብ ሀብታም፤ በድኩማን ብቻ የሚከበብ ባለ ሥልጣን፣ በተራዎች ብቻ የሚከበብ ዝነኛ፤ በማይማን ብቻ የሚከበብ ሊቅ እንደዚሁ ነው፡፡
በሀብት ውስጥ ጥቂት ድህነት፣ በሥልጣን ውስጥ ጥቂት ተዋርዶ፣ በዝና ውስጥ ጥቂት ተራነት፣ በጥጋብ ውስጥ ጥቂት ረሃብ ከሌለ ጣዕሙን ማወቅ አትችልም፡፡ የሚሞግትህና የሚከራከርህ፣ የሚተካከልህም ሳይኖር ብቻህን ባለሥልጣን ከሆንክኮ ወዳጅ አይኖርህም፡፡የሚኖርህ እንደ ባለዛር ዛር አንጋሽ ብቻ ነው፡፡ ከብበውህ ብቻ የሚያጨበጭቡ፡፡ የሚተካ ከልህና የሚመስልህ በሌለበት ባዕለ ጸጋ ከሆንክኮ አንተ አትለብስም የፋሽን ትርዒት ታሳያለህ እንጂ፤ አንተኮ አትበላም፤ የምግብ ኤግዚቢሽን ታቀርባለህ እንጂ፤ ሰዎች አድራሻቸውን ካንተ ቤት አጠገብ እያሉ ይናገራሉ፤ አንተ ግን ከማን አጠገብ አለሁ ትላለህ?»
ይኼ ሁሉ ግን የሰውዬውን ልብ አልሰበረውም፡፡ እርሱ ወርቁን ሊምነሸነሽ ቋምጧል፡፡
ጠቢቡ መላ ሰውነቱን ቀባው፡፡ «በል» አለው ጠቢቡ፡፡ «በል መድኃኒቱ ከነገ ጀምሮ ይሠራልሃል» ገንዘቡን ከፍሎ ወጣ፡፡ ሲመጣ የደከመውን ያህል ሲመለስ አልተሰማውም፡፡ ቀን አንዲት ደቂቃ ብቻ በሆነች ብሎ ተመኘ፡፡
አልተኛም፡፡ ሲገላበጥ ነው ያደረው፡፡ አይነጋ የለም ነጋ፡፡
ከአልጋው ወረደና መጀመርያ አልጋውን አየው፡፡ አልጋው ወርቅ ሆኗል፡፡ ሊያምን አልቻለም፡፡ ቤቱን ነካው፡፡ ቤቱ ከወርቅ የተሠራ ሆነ፡፡ በቤቱ ውስጥ እየተዘዋወረ ዕቃዎቹን ሁሉ ነካቸው፡፡ አንድም ሳይቀር የወርቅ ዕቃዎች ሆኑ፡፡
ከቤቱ ወጣና ጥቂት የወርቅ ብሮች ይዞ ገበያ ሄደ፡፡ ወርቅ ለብሷል፤ ወርቅ ተጫምቷል፡፡ ያዩት ሁሉ ተገረሙ፡፡ የሚያውቁት ሁሉ ግራ ገባቸው፡፡ ወደ አንድ ሱቅ ጎራ ብሎ የሚያስፈልገውን ሁሉ አዘዘ፡፡ ለመደገፍ ብሎ ባንኮኒውን ሲነካው ባንኮኒው ወርቅ ሆነ፡፡ የሱቁ ባለቤት በደስታ ሰከረ፡፡ ከሰውዬው ጋር ጭቅጭቅ ጀመሩ፡፡ ይህ ባንኮኒ የማን ነው? በመጨረሻ ባለ ሱቁ አሸነፈና ወሰደ፡፡ ያም ሰው የገዛውን ይዞ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ቤቱ ሲደርስ የገዛበትን ቀረጢት ሲያየው ወርቅ ሆኗል፡፡ ምግቡንም ሲያወጣው ወርቅ ሆኗል፡፡
እንደገና ተመልሶ ወደ ምግብ ቤት ገባ፡፡ ምግብ አዘዘ፡፡ መቀመጫውን ላለመንካት እየተጠነቀቀ ተቀመጠ፡፡ ምግቡ መጣለት፡፡ ዳቦውን ሊቆርሰው ሲጀምር ተለወጠና ወርቅ ሆነ፡፡ ይሄኔ አስተናጋጁ ማመን አቅቶት ጠጋ አለና ነፍሱ ስትመለስለት ዳቦውን ይዞ በረረ፡፡ ግራ ተጋባ፡፡ ቢያንስ ውኃ ጥሙን ለማርካት ብርጭ ቆውን ሲያነሳ ብርጭቆውና በውስጡ ያለው ውኃ ወርቅ ሆኗል፡፡
ወርቅ ይዞ ተራበ፡፡ ዝቅ ሲል የተቀመጠበት ወንበርም ወርቅ ሆኗል፡፡ የምግብ ቤቱ ባለቤት እርሱን ከወንበሩ ዘርግፎ ወርቅ የሆነውን ወንበር ይዞ በረረ፡፡
እዚያው እንደተቀመጠ ሰዎች መጡ፡፡ በተቀመጠበት አያሌ እንጨቶችን አመጡና ከመሩበት፡፡ ኡኡ እያለ እየጮኸ ማንም አልሰማውም፡፡ እነዚያ እንጨቶች ሁሉ ወርቅ ሆኑላቸው፡፡ እርሱ ግን ውጭ ነፍስ ግቢ ነፍስ መከራውን ሲያይ ቆየ፡፡ ሁሉም ወርቃቸውን እየያዙ ጥለውት ጠፉ፡፡
ሌሎች ሰዎችም መጡና ዕቃቸውን እንዲነካላቸው ሊወስዱት ያዙት፡፡ ሰዎቹ ግን እንደ ቆሙ ወርቅ ሆነው ቀሩ፡፡ ሌሎች ጓደዖቻቸውም ተሸክመው ወሰዷቸው፡፡ አሁን ሰዎች ይፈሩት ጀመር፡፡
ከምግብ ቤቱ በድካም መንፈስ ወጣና በኀዘን ወደ ቤቱ ሲያመራ አንድ ሰው በትልቅ ዱላ ከኋላው ገፈተረው፡፡ ተንደርድሮ የጠጠር ክምር ላይ ወደቀ፡፡ ጠጠሩም ወርቅ ሆነ፡፡ ሕዝቡም እየተሻማ ወሰደው፡፡ ከምግብ ቤቱ እስከ ቤቱ ድረስ ከአሥር ጊዜ በላይ ገፍትረው ድንጋይና እንጨት ላይ ጥለውት ነበር፡፡ እንዲያውም ይዘው ሊወስዱትም አስበው ነበር፡፡ ነገር ግን ወርቅ ያደርገናል ብለው ፈሩና ተውት፡፡
እርሱን ለመገፍተር እንጂ ከእርሱ ለመጠጋት የሚፈልግ ጠፋ፡፡ ቤቱ ደርሶ በሩን ዘጋና ተቀመጠ፡፡ ምን ይብላ፡፡ ሁሉም ወርቅ ሆኗል፡፡ ምን ይጠጣ? ሁሉም ወርቅ ሆኗል፡፡ ግራ ገባው፡፡ «ሰው እንዴት ወርቅ እያለው ይራባል» አለ ለብቻው፡፡ ቤቱ ከፊትና ከኋላ ይደበደባል፡፡ የከተማው ሰዎች ሁሉ የሆነውን ስለ ሰሙ ዕቃዎቻቸውን ወርቅ ለማድረግ ቤቱን ከብበውታል፡፡ የእርሱ ከተማ ብቻ ሳይሆን ወሬውን የሰሙ የሌሎች ከተሞች ሰዎችም ባገኙት መጓጓዣ ሁሉ ወደ እርሱ ቤት በመምጣት ላይ ናቸው፡፡
በሩ በኃይል ተመታ፡፡ ተነቀነቀ፡፡ ከዚያ በኃይል ተከፈተ፡፡ የሕዝብ ጎርፍ ወደ ቤቱ ፈሰሰ፡፡
አንዱ በእንጨት፤ ሌላው በልብስ፣ ሌላው በድንጋይ፣ ሌላው በቤት ዕቃ፣ ሌላው በገመድ፣ ሌላው በድመትና በአይጥ እየወረወረ ይመታው ጀመር፡፡ ሁሉም ነገር እርሱ ጋ ሲደርስ ወርቅ እየሆነ ይመለሳል፡፡ ያጋጠመው ተሽቀዳድሞ ይወስዳል፡፡ ሌሎቹ ደግሞ አስቀድሞ ነክቶ ወርቅ ያደረጋቸውን የቤቱን ዕቃዎች ያጓጉዛሉ፡፡
ውኃ ይላል፡፡ ራበኝ ይላል፤ ደከመኝ ይላል፡፡ ሞትኩ ይላል፡፡ ግን ማን ይሰማዋል፡፡
ያ ጠቢብ ያለው ትዝ አለው፡፡ «ምንም በማይበሉ ድኾች መካከል በምግብ ላይ አንተ ብቻ ከተኛህ፤ ድኾቹ በመጨረሻ አንተን ይበሉሃል፡፡ ምንም ሥልጣን በሌላቸው ሰዎች መካከል ሥልጣኑ አንተ ጋ ብቻ ካለ፤ ተራዎቹ ሰዎች የተከማቸውን ሥልጣንህን ሲፈልጉ አንተን ይገለብጡሃል፡፡ መናጢ ችግረኞች መካከል አንተ በወርቅ ከተንበሸበሽክ፣ ችግረኞቹ ሲመራቸው አንተን ይሸጡሃል፡፡ እና ብቻህን ሀብታም፣ ብቻህን ባለ ሥልጣን፣ ብቻህን ጥጋበኛ አትሁን» ብሎት ነበር፡፡ ግን አልሰማም፡፡
አንድ ክፉ ሰው ከመካከል ተነሣ፡፡
«እንዲህ ወርቅ በአንድ ሰው ላይ ብቻ ተከማችቶ ልንኖር አንችልም፡፡ ቆራርጠን እንካፈለውና በየሠፈራችን እናስቀምጠው፡፡ ከዚያ እያስነካን ወርቅ ማድረግ ነው፡፡ ለምን ወርቅ ፍለጋ እዚህ ድረስ እንደክማለን» ሁሉም በዚህ ተስማሙ፡፡ ግን ማን ይቅረበው፡፡ ሁሉም ራሱ ወርቅ ሆኖ ሌሎች እንዳይወስዱት ፈራ፡፡ ተንኮለኛ ደግሞ አጋዥ አያጣም፡፡ አንዱ ገመድ ቋጥሮ አመጣ፡፡ እንዳይነካው በእንጨት እየተከላከለ በእጅና በእግሩ ሸምቅቆ አስገባበት፡፡ ገመዱ ወርቅ ሆነ፡፡
ያን ጊዜ ሁሉም በየአቅጣጫቸው ጎተቱት፡፡ ሰውዬው ከአራት ተቆራረጠ፡፡ ሁሉም የደረሰውን ክፍል እያንጠለጠለ ወደየሠፈሩ ተጓዘ፡፡ ሌሎችም እንዲሁ ገመድ እያስገቡና ከሰውዬው እየቦጨቁ ወደየሠፈራቸው ሮጡ፡፡ በመጨረሻ ሰውዬው «ምንም» ሆኖ ቀረ፡፡
የሚያሳዝነው ግን ሕዝቡ ወርቅ መኖሩን እንጂ ወርቁ እንዴት እንደመጣ አያውቅም፡፡ መድኃኒቱን የሰጠው ጠቢብ ከሞተ በኋላ እንደማይሠራ እንደነገረው መንደርተኞቹ አልሰሙም፡፡ ያለውም አልቀረ በየመንደሩ የገባው የሰውዬው ቁርጥራጭ ምንም ሊሠራላቸው አልቻለም፡፡ ሰውዬው እርሱም አልተጠቀመም፤ ሕዝቡም አልተጠቀመም፡፡
ታምፓ፣ ፍሎሪዳ
© ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ የወጣ በመሆኑ በተመሳሳይ ኅትመት ላይ ባታውሉትይመረጣል፡