ለቤተ መጻሕፍትዎ
ባሕረ ሐሳብ
የቀመርና የሥነ ፈለክ ምሥጢር
አዘጋጅ፡– አለቃ ያሬድ ፈንታ ወልደ ዮሐንስ
የገጽ ብዛት፡– 214
ዋጋ፡– 50 ብር
ኅትመት፡– ፋርኢስት ትሬዲንግ
ዘመን፡– 2004 ዓመተ ሥጋዌ
ጥቂት ስለ ደራሲው፡– በ1915 ዓም የተወለዱት አለቃ ያሬድ በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት የአቡሻክር ሊቃውንት ዋናውና አንጋፋው ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ዋና ዋና ትምህርቶችን በሚገባ የተማሩት አለቃ ያሬድ ከቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅም ለአራት ዓመታት ተምረው ተመርቀዋል፡፡ አለቃ ያሬድ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ኮሌጅ ለ24 ዓመታት ባሕረ ሐሳብን አስተምረዋል፡፡አለቃ ያሬድ ከማስተማር በተጨማሪ ልዩ ልዩ ጥናታዊ ጽሑፎችን በማቅረብም ይታወቃሉ፡፡ ይኼኛው አራተኛው መጽሐፋቸው ነው፡፡
መጽሐፉ
መጽሐፉ ከቃላት መፍቻ ይጀምራል፡፡ ይኼም ስለ ባሕረ ሐሳብ ማወቅ ለሚፈልግ ሰው ከትምህርቱ ጋር የተያያዙትን ሥያሜ ቃላት (Terminologies) እንዲረዳና ንባቡና ምርምሩ ቀና እንዲሆንለት ይረዳዋል፡፡
ወደ መጽሐፉ ሲገቡ እውነትም ይህ ትምህርት ባሕር ነው የሚያሰኝ ነገር ይገጥማችኋል፡፡ እያንዳንዱን በዓልና ጾም ለመወሰን የተጠቀሙበት ቀመር (Formula) አንድን ዘመን ወደፊትና ወደ ኋላ ተጉዞ ለማግኘት የሄዱበት የስሌት መንገድ እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ በቀደምቶቻችን ዘንድ ስሌት የነበረውን ታላቅ ቦታ ያሳያችኋል፡፡
አበው ይጠቀሙባቸው የነበሩትን ሐሳበ ሳቤላን፣ ሐሳበ ጉንዳ ጉንዲን፣ የሐሳበ ግብፃውያንና ሐሳበ ቢዘንን እየተነተነ የእያንዳንዱን መነሻና ልዩነት ያትታል፡፡ ከዚህም አልፎ በጎንደር ዘመን በዐፄ ኢያሱ ጊዜ የተነሡ ሊቃውንት አራቱን ሐሳባት መርምረው ልዩነቶቻቸውን አንጥረው ያወጡበትን ምርምርም ይዟል፡፡
አለቃ ያሬድ የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመሮቹን ካስቀመጡ በኋላ ከ1984 ዓም ዕድሜ ከሰጠን እስከ 2480 ዓም ያለውን የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ሠንጠረዥ አዘጋጅተውልናል፡፡
የየኔታ ያሬድን መጽሐፍ እስካሁን ከተጻፉት የባሕረ ሐሳብ መጻሕፍት ልዩ የሚያደርገው ስለ ጨረቃ፣ ፀሐይና ከዋክብት መንገዶች የጻፉት ሐተታ ነው፡፡ በዚህ ሐተታቸው ላይ ጨረቃ በየት ወጥታ በየት እንደምትገባ፣ በእያንዳንዱ ጉዞዋ የሚኖራትን መጠን፤ ከፀሐይ ጋር ያላትን ማነስና መብለጥ እየተነተኑ አቅርበዋል፡፡ እንዲያውም ለጨረቃና ለፀሐይ ብርሃንን የሚያወጡበት እንደ ወንፊት ያለ ነገር አላቸው ይህም ምዕዛር ወይንም ስቁረት ይባላል ይሉና ለፀሐይ 595 ለጨረቃ ደግሞ 105 አላቸው፡፡ የፀሐይ ብርሃን ከጨረቃ የሚበልጠው በዚህ ምክንያት ነው ይሉናል፡፡ ይህንን ብለውም አያበቁም፡፡ እያንዳንዱ ምዕዛር በስንት ሰዓት እንደሚከፈት ያትታሉ፡፡
በ1 ሰዓት 98
በ2 ሰዓት 196
በ3 ሰዓት 294
በ4 ሰዓት 392
በ5 ሰዓት 490
በ6 ሰዓት 588 ይከፈታሉ ይላሉ፡፡ በቀትር ሰዓት ፀሐይ የሚያይለውም ብዙ ምዕዛራት በዚያ ጊዜ ስለሚከፈቱ ነው ማለት ነው፡፡ ከስድስት ሰዓት በኋላ ደግሞ የመዘጊያቸው ጊዜ ነው ይሉናል፡፡ መጀመርያ የተከፈተው በሰባት ሰዓት ይዘጋል፡፡ ከዚያ እንዲያ እያለ እስከ አሥራ ሁለት ሰዓት ይቀጥላል፡፡
አለቃ ያሬድ የጨረቃን ብርሃን በየሰዓቱ ለክተው የብርሃንዋን መጠን በሠንጠረዥ አቅርበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሊቃውንት እንዲህ የብርሃንን መጠን እስከ መለካት ደርሰው ነበር ማለት ነው፡፡
የአለቃ ያሬድ መጽሐፍ በፀሐይና በጨረቃ ብቻ አያቆምም፡፡ ወደ ከዋክብትም አልፎ የከዋክብትን ዓይነትና የአወጣጣቸውን ሁኔታ ከነ ስማቸው ይተነትናል፡፡ በየአንዳንዱ ወር የሚወጡ አሥራ ሁለት ከዋክብት መኖራቸውን፣ በእነርሱ ሥር የሚወጡ 28 ንኡሳን ከዋክብት መኖራቸውን ያትታሉ፡፡
አለቃ ከከዋክብት ወደ ነፋሳትም ይወርዳሉ፡፡ እንደ ሔኖክ አሥራ ሁለት ነፋሳት የሚነፍሱባቸው አሥራ ሁለት መስኮቶች መኖራቸውን ያትቱና እያንዳንዱ ነፋስ መቼ እንደሚወጣና ምን ይዞ እንደሚወጣም ይነግሩናል፡፡ ያንንም በሥዕል አሳይተዋል፡፡
የአለቃ ያሬድ መጽሐፍ እጅግ ጥልቅ ከሆነው ዕውቀታቸው የተቀዳ በመሆኑ ለእርሳቸው ትንሽ ለእኛ ግን ብዙ ነው፡፡ በተለይም ሐሳቡን በካርታ፣ በሥዕልና በሠንጠረዥ ለማስረዳት ያደረጉት ጥረት የሚመሰገን ነው፡፡
የዘጠና ዓመቱ አረጋዊ ሊቅ ወደ እግዚአብሔር ሳይሄዱ ቀድመን በተለይም በዚህ በዘመን አቆጣጠር ጉዳይ የሚነሡ ጥያቄዎችን በቀጥታ የሚመልሱበት፣ ሕዝቡም ጥያቄ የሚያቀርብበት መድረክ ቢፈጠር፤ ያም መድረክ በቪዲዮ ተቀርፆ አለቃን ከነ ሁለመናቸው እንድናስቀራቸው ቢደረግ መልካም ነው፡፡
እንዲህ ያሉ ሊቃውንትን ማጣት አንድ ቤተ መጻሕፍት እንደ ማጣት ነውና በተለይም ልጃቸው ሔኖክ ያሬድ አለቃ ነገ ተጠርተው ሲሄዱ ነፍሳቸው ከእግዚአብሔር ጋር እንደምትሆን ሁሉ ዕውቀታቸው ከኛ ጋር እንዲቀር የሚችለውን ሁሉ እንዲያደርግ አደራ እንላለን፡፡
