በጉራፋርዳ ወረዳ ሁለት ቀበሌዎች 22 የአማራ ተወላጆች ቤቶች ተቃጠሉ

የደቡብ ክልል መስተዳድር ማንም ሕጋዊ ሰው ከክልሉ አልተፈናቀለም በሚል ሰሞኑን መግለጫ ቢሰጥም መጋቢት 29 ለ30 አጥቢያ በጉራፋርዳ ሁለት ቀበሌዎች 22 ቤቶች መቃጠላቸውን፣ ስምንት ወፍጮዎችም ተነቃቅለው መወሰዳቸው የመኢአድ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡

የደቡብ ክልል ፕሬዚዳንት አማካሪ አቶ አሚሳ ሚልኮ በበኩላቸው፣ የተፈናቃዮችን ጉዳይ የሚያጣራ ኮሚቴ ስለመቋቋሙ የሚያውቁት ነገር አለመኖሩን ለሪፖርተር ገልጸዋው፣ “እውነታው ምንድነው ለሚለው በቂ መረጃ አለን” የሚሉት አቶ አሚሳ፣ ክልሉን ለቀው እንዲወጡ የተደረጉት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ አካባቢው መጥተው ደን በመጨፍጨፍ በሕገወጥ መንገድ የሰፈሩ ሰዎች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

“ዝም ተብሎ የሰው ጓሮ አይገባም፤ መሬት ጠቧቸው የሚመጡበት ሁኔታ ካለ ሁለቱ ክልሎች [አማራና ደቡብ ክልሎች] ሊወያዩ ይገባል፤” በማለት ሰፈራ በሕጋዊ መንገድ መካሄድ እንዳለበት ይናገራሉ፡፡

እርሳቸው እንደሚሉት፣ በጉራፋርዳ ወረዳ በሕጋዊ መንገድ መሬት ተረክቦ በአካባቢው ሲኖር የነበረ አንድም ሰው እንዲፈናቀል አልተደረገም፡፡ “አካባቢውን እንዲለቁ የተደረጉት ከየካቲት ወር በኋላ [በያዝነው ዓመት] በኋላ የመጡ ናቸው፡፡ ነባር ሰዎች ተፈናቀሉ የሚባለው ስህተት ነው፤” ብለዋል፡፡