ፍርድ ቤቱ በዘሪሁን ሙላቱ ላይ ሦስተኛ ቀጠሮ ሰጠ

 (ደጀ ሰላም፤ ሰፕቴምበር 1/2001፤ ነሐሴ 26/2002 ዓ.ም):- የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞችበሚለው መጽሐፍሳቢያ የስም ማጥፋት ክስ የቀረበበትን የሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱን ጉዳይ የሚመለከተው በአዲስ አበባ አስተዳደር የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት በተጠርጣሪው ላይ የሚሰበሰቡት መረጃዎች እንዲጠናቀቁ በማሳሰብ ለጳጉሜን ሁለት ቀን 2002 .ም ጠዋት ሦስተኛ ቀጠሮ ሰጠ፡፡
በትንትናው ዕለት ረፋድ ላይ ችሎቱ ሲሠየም የግል ተበዳይ ከተባሉት ከሳሾች መካከል ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ የቀረቡ ሲሆን መርማሪው ፖሊስ እና ዐቃቤ ሕጉ የደረሱበትን የምርመራ ሂደት ለፍርድ ቤቱ በቃል አስረድተዋል፡፡ የቀረበው ገለጻ፣ ‹‹መጽሐፉ የታተመበትን ማተሚያ ቤት እየደረስንበት ነው፤ ይህን የሚያመለክቱን ፍንጮች አግኝተናል፡፡ ከዚያ በፊት ተጠርጣሪው በዋስ ቢለቀቅ መረጃ ሊያጠፋብን ስለሚችል ተጨማሪ ቀን እንዲፈቀድልን እንጠይቃለን፤›› የሚል ነው፡፡ ተጠርጣሪው ጸሐፊ በበኩሉ በእርሱ ብቻ የሚረዱ ታማሚ እናት ስላሉት የዋስ መብቱ ተጠብቆለት በውጭ ጉዳዩን መከታተል እንዲችል ፍርድ ቤቱን በድጋሚ ጠይቋል፡፡ በመጨረሻ ዳኛው በሰጡት ትእዛዝ፣ ‹‹ከተፈጸመው ጥፋት ጋራ ተያያዥነት ከሌለህ በአጭር ቀን ነጻነትህ እንዲረጋገጥ እናደርጋለን፡፡ ፖሊስ እና ዐቃቤ ሕግ ማስረጃ አለን እያሉ ምንም ልናደርግልህ አንችልም፤›› በማለት ለጳጉሜን ሁለት ቀን 2002 .ም የምርመራው ሂደት ተጠናቅቆ ማስረጃው እንዲቀርብ በጥብቅ በማዘዝ ተለዋጭ ቀጠሮ ከሰጡ በኋላ ችሎት መልስ ሆኗል፡፡