ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ወደ ሀገር ቤት ተመለሱ
(ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 27/2010)፦ በጀርመን ሀገር ሕክምና ሲከታተሉ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ሕክምናቸውን ፈጽመው ወደ ሀገር ቤት ተመለሱ።
ብፁዕነታቸው ለሚያሰቃያቸው የጀርባ ሕመም መፍትሔ ለማግኘት ቀደም ብሎ በግሪክ ከዚያም ደግሞ በጀርመን ሲታከሙ ቆይተው ባለፈው ሐሙስ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ በቅተዋል። ብፁዕነታቸው አሁን በተሻለ ጤንነት ላይ የሚገኙ ሲሆን ምርኩዛቸውን ተደግፈው ለመንቀሳቀስም ችለዋል።
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ወቅት ካሏት በሐዋርያነታቸው ከሚሰከርላቸው ደጋግ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል አረጋዊ አባት የሆኑት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በግሪክ እና በጀርመን የሚገኙ ክርስቲያኖች ባደረጉላቸው ርዳታ ከጥሩ ጤንነት ላይ ለመድረስ ችለዋል።
እንደሚታወቀው በቤተ ክህነታችን የሕክምናም ሆነ የጤና ኢንሹራንስ ስለሌለ አባቶች (በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ) በሚያሳዝን መልኩ እያለቁ ነው። ለምሳሌ በቅርብ ጊዜ ያረፉትን አቡነ መልከ ጼዴቅን ማንሳት ይቻላል።
ብፁዕነታቸውን ሳይታክቱ ያገለገሉት ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ሰው ስለሆኑ ከብፁዕነታቸው ትልቅ በረከት እና ረድኤት እንደሚያገኙ ብታውቅም “ደጀ ሰላም” በግሪክ እና በጀርመን ያሉትን ክርስቲያኖች በሙሉ ከልብ ታመሰግናቸዋለች።
ይህንን ፎቶግራፍ የላኩልንንም ከልብ እናመሰግናለን።
ቸር ወሬ ያሰማን፣
አሜን