“ነብይ በአገሩ አይከበርም” … እውነት!? (ማስተዋል አዳነ)

ክፍል አንድ (ማስተዋል አዳነ)

ጊዜው በአገራችን ክረምት ሊገባ ጥቂት ጊዜያት የቀሩበት ወቅት ነበር፤ የአሁኑ ክረምት። ወደአገር ቤት ለመሄድ የወሰንኩት ቤተሰብ፣ ጓደኛና ዘመድ ለመጠየቅና በአጠቃላይ የአገራችን የኑሮ ሁኔታ በጣም ስለናፈቀኝ፤ ይህንን ደግሞ ከተወሰነ አመት የትምህርት ቆይታ በኋላ ተመልሼ ማየት አለብኝ የሚል ውሳኔ ላይ ስለደረስኩ ነበር። ተማሪ ስለሆንኩና የእረፍት ጊዜዬንም በዚሁ አጋጣሚውን መጠቀሙ ጥሩ አማራጭ ስለሆነ ከፍራንክፈርት ወደአዲስ አበባ ትኬት ቆርጬ ግንቦት መጨረሻ ላይ ወደአገር ቤት ለመሄድ ተሰናዳሁ። የበረራ ቀን ሰኞ ነበር።