ኢትዮጵያ ውስጥ ኦስካር ሮሜሮዎች፣ አርተር ሱሌማኖቮች፣ አሊ ሲስታኒዎች አሉን?
ከግርማ ካሳ
እሁድ እለተ ሰንበት ቀን ነበር። አምላካቸዉንና ፈጣሪያቸዉን ሊያመሰግኑ ምእመናን የቤተ ክርስቲያኒቱን አዳራሽ አጣበዉታል። በአዳራሹ የነበረዉ ምእመን ፊቱን ወደ መንበረ ታቦቱ አዙሯል። በመንበረ ታቦቱ በቀኝና በግራ በኩል ነጭ የለበሱ ዲያቆናት ቆመዋል። በዲያቆናቱ መካከል ከመንበረ ታቦቱ በኋላ ምእመኑን ፊት ለፊት የሚያዩ አንድ የእግዚብሄር ሰዉ ይታያሉ። እኝህ ሰዉ በመንበረ ታቦቱ ላይ የነበረዉን ሕብስት በሁለት እጃቸዉ አነሱ። ወደ ሰማይ ዘርግተዉ ሕብስቱን መባረክ ጀመሩ። በእጆቻቸዉ ወደ ላይ ከፍ ያደረጉትን ህብስት ወደ ቦታዉ ሳይመልሱት፣ ድንገት ሕብስቱም እርሳቸዉም መሬት ላይ ወደቁ።
እኝህ ሰዉ ቅዳሴ እየቀደሱ ነበር። ሕብስቱም የጌታ ሥጋ (ቅዱስ ቁርባን) ነበር። ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዉስጥ ከሚገኝ የከፍታ ቦታ የተተኮሰ ጥይት የእኝህ የእግዚአብሄር አገልጋይ ደረት ላይ አረፈ። የተኮሱት ታጣቂዎች ወዲያዉ ስፍራዉን ለቀዉ ጠፉ። ህዝቡ ተደናገጠ። ለቅሶና ዋይታ አዳራሹን አቀለጠዉ።
ቅዳሴ ሲያስቀድሱ በጥይት የተገደሉት እኝህ የእግዚብሄር ሰዉ፣ የኤልሳልቫዶር (ላቲን አሜሪካ ዉስጥ ያለች አገር ናት) ሊቀ ጳጳስ ኦስካር ሮሚሮ ነበሩ። ኦስካር ሮሚሮ በኤልሳልቫዶር የተስፋፋዉን ኢፍትሃዊነት፣ በመንግስት የሚደረገዉን ሽብርና ግድያ፣ በአገሪቱም የነበረዉን የከፋ ድህነት አጥበቀዉ የሚያወግዙ ታላቅ የእግዚአብሄር ሰዉ ነበሩ። የሚመሩበትና የሚሰብኩት ወንጌል የፍትህ መጽሃፍ፣ የሚከተሉትና የሚያመልኩት ጌታ የፍትህ አምላክ መሆኑን በመረዳታቸዉ፣ ይሉኝታ፣ ፍርሃት ሳይዛቸዉ፣ ጥቅምና ምቾት ሳያታልላቸዉ ለፍትህ የቆሙ ነበሩ።
በአሜሪካዉ ዴሞክራስቲኩ ፕሬዘዳንት ጂሚ ካርተር ይደገፍ የነበረዉ፣ የወቅቱ የኤልሳልቫአዶር ወታደራዊ ጁንታ፣ እኝህን ሰዉ በመግደል ዝም ለማሰኘት የመረጠዉ፣ የሊቀ ጳጳስ ኦስካር ጠንካራ የፍትህ አቋም ስላልተመቸዉና ስላሰጋዉ ነበር።
ኦስካር ሮሜሮ ለእዉነት፣ ለፍትህ፣ ለድሆች በመቆማቸዉ በወቅቱ ጉልበተኞች በተተኮሰ ጥይት እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ 1981 ዓ.ም ነበር የወደቁት። ኦስካር ሮሜሮ እንደ ሌሎች አደርባይ የሃይማኖት መሪዎች ከመንግስት ባለሥልጣናት ጋር ተሻርከዉ፣ የሕሊናቸዉንና የአምላካቸዉን ድምጽ ጆሮ ዳባ ልበስ ብለዉ መኖር ይችሉ ነበር። ነገር ግን የእግዚብሄር ሰዉ ምን መሆን እንዳለበት ሕይወታቸዉን በመስጠት ያሳዩ ታላቅና የተከበሩ የዘመናችን ሰዉ ነበሩ።
በሩሲያ በምትገኝ፣ ነዋሪዎቿ 90% ሙስሊሞች በሆኑባት፣ ዳጊስታን በምትባል ክፍለ ሃገር፣ ብዙ አባላትን ያቀፈች አንዲት «ሆሳእና» የምትባል የፔንቴኮስታል ቤተ ክርስቲያን አለች። የቤተ ከርስቲያኒቱ አባላት፣ በቤተ ክርስቲያናቸዉ አዳራሽ ከመዘመርና ከማምለክ በተጨማሪ፣ በሥራቸዉም እምነታቸዉን የሚገልጹ ክርስቲያኖች ነበሩ። በእሥር ቤት የሚገኙ በርካታ የዳጊስታን ነዋሪዎችን እየጎበኙ መጠነ ሰፊ የሰብዓዊነት አገልግሎት ይሰጡ ነበር። ክርስትና መስቀል ወይንም መጽሃፍ ቅዱስ ይዞ መዞር፣ ጠዋትና ማታ ቤተ ክርስቲያን መዋል ፣ መስቀል ይዞ እያማተቡ በስመ አብ ወይንም ደግሞ መጽሃፍ ቅዱስ ወደ ላይ እያነሱ «በኢየሱስ ስም» ማለት ብቻ ሳይሆን፣ «ታምሜ አልጎበኛችሁም፤ ታስሬ አልጠየቃችሁኝም፣ ታርዤ አላለበሳችሁኝም፣ ተርቤ አላበላችሁኝም» እንደሚለዉ መጽሃፉ፣ የተጠቁትን፣ የተገፉትን፣ የወደቁትን መመልከትና ማንሳት፣ ለመበለቲቱ መሟገት፣ ለድሃ አደጉ መፍረድ እንደሆነ የገባቸዉ ክርስቲያኖች ነበሩ።
የሆሳዕና ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ይህን መሰል የተከበረ ሰብዓዊ አገልግሎት ከመስጠት ባሻገር፣ የቤተ ክርስቲያኒቷ መጋቢና ፓስተር፣ በክልሉ ባለሥልጣናት የሚደረጉ ግፎችንና ወከባዎችን በግልጽና በድፍረት ይቃወሙና ያወግዙ ነበር። ፍትህ ሲዛባና ፍትህ ሲረገጥ ማየት የክርስትና እምነትን የሚጻረር በመሆኑ፣ ለፍትህ ያልቆመ ክርስቲያን ክርስቲያን ሊባል ስለማይችል፣ ፓስተሩ ለጥቅምና ለጊዚያዊ ከበሬታ ሲሉ እምነታቸዉን አመቻምቸዉ ከመኖር፣ እዉነትን ተናግረዉ የሚመጣዉ ለመቀበል ወሰኑ።
ከአራት ሳምንት በፊት ነዉ ፣ ጁላይ 15 ቀን እኝህ የሆሳእና ፔንቴኮስታል ቤተ ክርስቲያን መጋቢ፣ ፓስተር አርተር ሱሌማኖቭ ከመኪናቸዉ ሲወጡ በታጣቂዎች የተገደሉት። የክልሉ ባለሥልጣናት በድርጊቱ እንደሌሉበት ይናገራሉ። ነገር ግን ከእኝህ ፓስተር አንደበት የሚወጡት የተከበሩ ቃላት እንደ ጦር ስላስፈራቸዉ፣ እርሳቸዉን ዝም ለማሰኘት ያደረጉት ሰይጣናዊ ድርጊት እንደሆነ ይታመንበታል። ፓስተር ሱሌማኖቭ ገና አርባ ዘጠኝ አመታቸዉ ነበር።
ሳዳም ሁሴን በአሜሪካኖች ወረራ ከስልጣን ተወግዷል። የሳዳም ሁሴንን መዉደቅ ተከትሎ በኢራቅ አንዳንድ ኃይሎች ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ። ከተለያዩ ቡድኖች የተወጣጣ ጊዚያዊ መንግስት ተቋቋመ። ኢያድ አላዊ የመጀመሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዉ ተሾሙ። እንደ ተጠበቀዉ ግን ሁኔታዎች ሊረጋጉ አልቻሉም። በአል ሳዳር የሚመሩት የሺያ ቡድኖች በአሜሪካኖች የሚደገፈዉ ጊዜያዊ መንግስት ላይ አመጹ። አሜሪካኖች ከአልካይዳና ከሱኒ ተዋጊዎች ጋር ብቻ ሳይሆን ከሺሃዎች ጋርም ፍጥጫ ገጠማቸዉ። ብዙ ጥረቶች ተደረጉ ሊሳካ አልቻለም። በመጨረሻ በናጃፍ ከፍተኛ ዉጊያ ተከፈተ።
ጦርነት መከፈቱን እንደሰሙ፣ የኢራን መንፈሳዊ አባት አያቶላ አሊ አልሲስታኒ ለሕክምና ከሄዱቡት ከለንደን፣ ወዲያዉ ተመለሱ። የኢራቅ ጊዚያዊ መንግስት ባለሥልጣናትን እንዲሁም የአልሳዳርን ቡድን እንደ አባት አነጋገሩ። በእኝህ የመንፈሳዊ አባት መሪ ምክርና ቁጣ ጦርነቱ ቆመ። ተኩስ አቁም ታወጀ። ናጃፍ ተረፈች።
አያቶላ አል ሲስታኒ ዝም ብለዉ ሊቀመጡ ይችሉ ነበር። ነገር ግን እንደ ሃይማኖት መሪነታቸዉ ማስታረቅ፣ በተቃራኒ ወገን ያሉትን ወደ ኣንድ ማምጣት እንዳለባቸዉ የተረዱ ታላቅ ሰዉ ነበሩ።
ኢትዮጵያ ዉስጥ ኦስካር ሮሜሮዎች፣ አርተር ሱሌማኖቮች፣ አሊ ሲስታኒዎች አሉን? በሰዉ ዘንድ ተቀባይነት ያላቸዉ፣ ለጥቅማቸዉ ያላደሩ፣ ለፍትህ የቆሙ፣ እግዚአብሄርን እንጂ ሰዉን ወይንም ባለሥልጣናትን የማያገለግሉ የእግዚአብሄር ሰዎች አሉንን ? አዎ የኃይማኖት መሪዎች አሉን። ነገር ግን የሉንምም!
በቅርብ የወጣዉ የሕዝብ ቆጠራ እንደሚያመልክተዉ በአገራችን ኢትዮጵያ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስቲያን አማኞች ወደ 43 በመቶ ይጠጋሉ። በሁለተኛነት ሙስሊም ወገኖቻችን በሰላሳና በአርባ በመቶ መካከል ሲሆኑ የወንጌላዉያን ቤተ ክርስቲያን አማኞች (ፕሮቴስታንት) ወደ 19 በመቶ ደርሰዋል። ካቶሊኮች በአለም ካሉ ክርስትቲያኖች በአንደኝነት የሚቆጠሩ ሲሆኑ ኢትዮጵያ ዉስጥ ግን 0.7% ብቻ ናቸዉ። ስናጠቃልለዉ ወደ 97% በመቶ የአገራችን ሕዝብ ክርስቲያን ወይንም ሙስሊም ነዉ። በሌላ አባባል «እግዚአብሄርን አምናለሁ፣ ኃይማኖት አለኝ» የሚል ነዉ።
ምርጫ 2002 ሊደረግ ጥቂት ቀናት ሲቀሩ፣ በቴሌቭዥን እንዳየነዉ፣ ካባ የለበሱ፣ መስቀል የያዙ፣ አንገታቸዉ ላይ ነጭ መቀነት ያደረጉ፣ የኃይማኖት መሪዎች ነን የሚሉ ብዙ አሉ። ነገር ግን እንደ ሊቀ ጳጳስ ሮሜሮና ፓስተር ሱሌማኖቭ ለፍትህ፣ ለተጠቃዉ፣ ለተገፋዉ ሲቆሙ አላየንም። በኢራቅ አያቶላ አል ሲስታኒ እንዳደረጉት በአገራችን የሰፈነዉ የፖለቲካ ቀዉስ ይወገድ ዘንድ፣ ኢትዮጵያዊያን እንደ ወንድማማቾች ይቀባበሉ ዘንድ፣ አንዳቸዉ በሌላቸዉ ላይ ከመጨከን ይቆጠቡ ዘንድ፣ ፍቅር በምድራችን ይሰፍን ዘንድ ለእርቅ ሲሰሩ አላየናቸዉም። በወንጌል እንደተጻፈዉ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲናገር « የሚያስታርቁ ብጹዓን ናቸዉ» ነበር ያለዉ። ነገር ግን እነዚህ መሪዎች እንኳን ሌሎችን ሊያስታርቁ ከራሳቸዉ ጋር መታረቅ ያልቻሉ መንፈሳዊ መሪዎች እንደሆኑ ነዉ እያየን ያለነዉ።
በአገራችን ዜጎች ይገደላሉ። የኢሕአዴግ አባል ስላልሆኑ ከሥራ ይባረራሉ። ያለ ምንም ወንጀል ፍርድ እየተጣመመ ይታሰራሉ። ሙስናና ሌብነት ከላይ ወደ ታች ተንሰራፍቷል። ካልሰረቁ፣ ጉቦ ካልበሉ፣ የኢሕአዴግ አባል ካልሆኑ፣ ከባለሥልጣናት ጋር ዝምድና ከሌላቸዉ፣ ወይንም ዉጭ አገር ዘመድ ከሌላቸዉ በስተቀር በንጹህ መንገድ ኢትዮጵያዉያን ሰርተዉ ትልቅ ደረጃ መድረስ የሚችሉበት ሁኔታ የለም። የ99.6 በመቶ የምርጫ ዉጤት እንደሚያመለክተዉ ሰለሳ አመታት ወደ ኋላ፣ ወደ ፍጹም አምባገነንነት እየሄድን ነዉ። በዚህ ሁኔታ የሞራል ድምጽ ሆነዉ፣ «የሚደረገዉ ነገር ትክክል አይደለም» የሚሉ የሃይማኖት አባቶችን አናይም።
በወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ እየደረሰ ያለዉን ግፍ በምሳሌነት መጥቀስ ብቻ ይበቃል። የአሜሪካና የአዉሮፓ መንግስታት፣ በርካታ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ፣ የተባበሩት መንግስታት፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ በአገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የሕሊናና የፖለቲካ እሥረኛ እንጂ የሕግ እሥረኛ እንዳልሆነች እየገለጹ፣ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እንድትፈታ እየጠየቁ ባለበት ሁኔታ፣ የሃይማኖት አባቶቻችን ግን አንድም ቃል ሲተነፍሱ አልሰማንም። ደፍረዉ አራት ኪሎ ያሉ ባለሥልጣናትን ለመገሰጽ ሆነ ለመናገር አልደፈሩም። ይልቅስ ይግረመንና ከኢሕአዴግ ባለሥልጣናት ጎን ተቀምጠዉ፣ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ያልሆነዉ ምርጫ ተቀባይነት እንዲኖረው ለማገዝ መግለጫዎች ሲሰጡ ነዉ የሰማናቸዉ። የምናየዉ ለራሳቸዉ ክብር ሃዉልት ሲያሰሩ ነዉ።
ከሶስት ሺህ አመታት በፊት በእሥራዔል መንፈሳዊ መሪ የነበሩት ሊቀ ካህኑ ኤሊና ሁለት ካህናት ልጆቹ ፊንሃስና አፍኒን ነበሩ። ፊንሃስና አፍኒን በቀን የካህን ካባ ለብሰዉ መሥዋእት ያቀርባሉ። በማታ ግን ታቦቱ ባለበት በመቅደስ ዉስጥ ያመነዝራሉ። የእግዚአብሄር ቃል ፍጹም በነዚህ አገልጋይ በሚባሉ ሰዎች ዘንድ የተናቀ ነበር።
እግዚአብሄር መሃሪ አምላክ ነዉ። ነገር ግን መጽሃፍ እንደሚል የሚባላም እሳት ነዉ። የእግዚብሄር ምህረት ታላቅና ዘላለማዊ ብትሆንም በሌላ በኩል ደግሞ ይች ምህረት አይዘበትባትም።
ያኔ በኤሊ ዘመን የእግዚአብሄር የፍርድና የቁጣ በትር ወረደች። በአንድ ቀን ፊናሃስን አፍኒን ተገደሉ። አባታቸዉም ኤሊ የልጆቹን መሞት ሲሰማ መጽሐፍ «ዔሊ በቅጥሩ በር አጠገብ ከተቀመጠበት ወንበር ላይ በጀርባዉ ወደቀ፤ እርሱም ያረጀነ ሰዉነቱም የሚከብድ ስለ ነበር፣ አንገቱ ተሰብሮ ሞተ» እንዳለዉ ደንግጦ ወድቆ ሞተ። እግዚአብሄር እራሱ የነዚህን አደርባይ ካሃናት ፍጻሜ ደነገገ።
የእግዚአብሄርን ቃል ንቀዉ ፣ የራሳቸዉን ክብር ለሚፈልጉ፣ በእግዚአብሄር ስም ለሚነግዱ፣ የተቀመጡበትን የተከበረ ወንበር ለሚያቀሉና ጥቅማቸዉን ለሚያሳድዱ የዘመኑ የአገራችን የሃይማኖት አባቶች «ዎ» እላለሁ። ለድሃና ለተገፋዉ የሚያስበዉ የዘላለም አምላክ እግዚአብሄር የፍርድ በትሩን በርግጥ የሚያነሳበት ጊዜ ይመጣል። ለነርሱም ክብር ያሰሩት ሃዉልት ናቡከደነጾር በሕሎሙ እንዳየዉ ምስል፣ ወይንም በደርግ ጊዜ በአይናችን እንዳየነዉ እንደ ቭላድሚር ሌሊን ሃዉልት ይፈራርሳል።
በሊቀ ካህኑ ኤሊ ምትክ፣ በፈሪሃ እግዚአብሄር የተሞላ፣ የእግዚአብሄርን ፊት በትህትና የሚፈልግ፣ ለእዉነት የቆመ፣ ፍትህን የማያዛባ፣ የሃናና የሕልቃና ልጅ ሳሙዔል እንደመጣ ሁሉ፣ የኢትዮጵያን ሕዝብ በእግዚአብሄር ቃል የሚያቀኑ፣ የኦስካር ሮሚሮና አርተር ሱሌማኖቭ አይነት ሃቀኛ፣ አይበገሬ፣ ታማኝ የእግዚአብሄር አገልጋዮች እግዚአብሄር ይስጠን!