የቀድሞው የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ዋና ጸሐፊ አረፉ

(ሪፖርተር) — የቀድሞው የሕፃናት ኮሚሽን ኮሚሽነር፣ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ዋና ጸሐፊ የነበሩት ኮሚሽነር ተሠራ ወርቅ ሽመልስና የኢትዮጵያ መንገዶች ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር መስፍን ኃይሌ ሥርዓተ ቀብር ከትናንት በስቲያ ተፈጸመ፡፡ ላለፉት አምስት አሠርት በተለያዩ ሰብዓዊና አገራዊ ጉዳዮች ከመንግሥት ከፍተኛ ሹምነት እስከ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መሪነት ያገለገሉት ኮሚሽነር ተሠራ ወርቅ፣ በተለይ በ1960ዎቹና 70ዎቹ በአገሪቱ ተከሥቶ የነበረውን የተፈጥሮ አደጋ ለመቋቋም ከተሰማሩት ግንባር ቀደምት መካከል አንዱ እንደነበሩ ከሕይወት ታሪካቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡

በቀይ መስቀል ማኅበር ዋና ጸሐፊነት ዘመናቸው የደም ባንክን ያቋቋሙት አቶ ተሠራ ወርቅ፣ ከነበሩባቸው ኃላፊነቶች መካከል የልጆች፣ ወጣቶችና ቤተሰብ ደኅንነት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የቴርዴስ ሆምስ የምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ፣ የዓባይ (ናይል) ተፋሰስ አገሮች የዕርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ሰብሳቢ ሆነው ያገለገሉበት ይገኙባቸዋል፡፡

ከአባታቸው አቶ ሽመልስ ዘነበወርቅና ከእናታቸው ወ/ሮ አፀደማርያም ቸርነት ጥቅምት 30 ቀን 1939 ዓ.ም. በሐረር ከተማ የተወለዱት ኮሚሽነር ተሠራ ወርቅ፣ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርታቸውን በሐረር ስዊድን ሚሽን፣ ሁለተኛ ደረጃን በአዲስ አበባ ኮከበ ጽባሕ ትምህርት ቤት ሲከታተሉ፣ ከንግድ ሥራ ኮሌጅ በ1957 ዓ.ም. ተመርቀዋል፡፡

ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በአገር ውስጥና በውጭ አገር ሕክምና ሲከታተሉ የነበሩት ኮሚሽነር ተሠራ ቀብራቸው ጥር 28 ቀን 2004 ዓ.ም. በሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡ ኮሚሽነር ተሠራ ወርቅ የአንዲት ሴትና አንድ ወንድ ልጆች አባት ነበሩ፡፡

በተያያዘ ዜና በሐምሌ ወር 2003 ዓ.ም የተቋቋመው የኢትዮጵያ መንገዶች ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር መስፍን ኃይሌ፣ ጥር 27 ቀን 2004 ዓ.ም አርፈው ጥር 28 ቀን 2004 ዓ.ም የቀብር ሥርዓታቸው በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡

ኢንጂነር መስፍን ከ1981 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሐምሌ ወር 2003 ዓ.ም ድረስ በኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን በተለያዩ ከፍተኛ ኃላፊነቶች የሠሩ መሆናቸውን ከሕይወት ታሪካቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡ በቀብራቸው ሥነ ሥርዓት ላይ አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳን ጨምሮ በርካታ የመንግሥት ባለሥልጣናት ተገኝተዋል፡፡