የኢንቨስትመንት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ከኃላፊነት ለቀቁ

የኢትዮጵያ ኢንቨሰትመንት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ለረዥም ዓመታት ያገለገሉት አቶ አቢ ወልደመስቀል ከኃላፊነታቸው ለቀቁ፡፡

ታማኝ የዜና ምንጮች ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ኅዳር 26 ቀን 2004 ዓ.ም. አቶ አቢ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በፃፉት ደብዳቤ በራሳቸው ፈቃድ ሥራቸውን ከጥር 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ መልቀቅ እንደሚፈልጉ ገልጸው መልቀቂያ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ጥያቄያቸው ተቀባይነት ማግኘቱን የሚገልጽ ደብዳቤ ሐሙስ ዕለት ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፊት ቤት እንደደረሳቸው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

አቶ አቢ በውጪ አገር የሚገኝ በአንድ ዓለም አቀፍ ድርጅት ውስጥ ሥራ ማግኘታቸውን የገለጹት ምንጮች፣ በቅርቡ ወደዚያው እንደሚያቀኑ ተናግረዋል፡፡

አቶ አቢ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲን በተለያዩ ኃላፊነቶች ለ20 ዓመታት ያህል አገልግለዋል፡፡ አቶ አቢ መሥርያ ቤቱ ሲቋቋም በመምሪያ ኃላፊነት ሥራቸውን የጀመሩ ሲሆን በመቀጠል ምክትል ዋና ሥራ አሰኪያጅ ሆነው አገልግለዋል፡፡ መሥሪያ ቤቱ ወደ ኮምሽንነት ሲቀየር ምክትል ኮምሽነር ሆነው ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡

በወቅቱ ዋና ኮምሽነር የነበሩት አቶ ታደሠ ኃይሌ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው ሲሾሙ አቶ አቢ ወደ ዋና ኮምሽነርነት ተሸጋግረዋል፡፡ በመቀጠልም መሥርያ ቤቱ ወደ ኤጀንሲነት ከተቀየረ በኋላ እስከአሁን በዋና ዳይሬክተርነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ አቶ አቢ ለመሥሪያ ቤቱ ባበረከቱት የረዥም ጊዜ አገልግሎት ከመንግሥት ምስጋና እንደተቸራቸው ምንጮች አክለው ገልጸዋል፡፡