የሒላሪን እውነቶች፤ለኛ ውሸታሞች

ሉሉ ከበደ

ቀኑን በስራ የዛለ ሰውነቴን ላሳርፍ አልኩና፤ የሁለት ዓመት ህጻን ልጄ አልፋን ይዤ ወደ መኝታ ቤት ገባሁ። ደንገዝገዝ ያለ ውሀ ሰማያዊ ብርሀን የሚሰጠውን የመኝታ ሰዓት መብራት አበራሁና በጀርባዬ አልጋ ላይ ተንጋለልኩ። ልጄ አልፋን ከአዲሷ አሻንጉሊቷ ጋር ደረቴ ላይ አድርጌያት፤ እሷም ከደረቴ ወደ አልጋው፤ ካልጋው ወደ ደረቴ እየተመላለሰች ባሻንጉሊቷ ስትጫወት፤ ቀኝ እጄን ግንባሬ ላይ አሳረፍኩ። ትራሴን ከፍ አድርጌ፤ አራት ባራት በሆነችው መኝታ ቤት ውስጥ ከፊት ለፊቴ ግርግዳ ላይ የተሰቀሉ ስዕሎችን እመለከት ጀመር። ከሁሉ ጎልቶ የሚታየው በሀገሬ ባንዲራ ከፈፍ ዙሪያውን ተሰግጦ ያማረው ትልቁ የኢትዮጵያ ካርታ ነበር።