አማርኛ በአፋር ክልል ከስራ ቋንቋነት ሊቀየረ ነው
(Reporter) — ላለፉት 20 ዓመታት የአማርኛ ቋንቋን የሥራ ቋንቋው አድርጎ ሲጠቀም የቆየው የአፋር ክልል መንግሥት፣ በቅርቡ የአፋርኛን ቋንቋ የክልሉ የሥራ ቋንቋ አድርጎ ለመጠቀም ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አስታወቀ፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ተጠሪ አቶ ጠሃ አህመድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በቅርቡ የክልሉ የሥራ ቋንቋን አፋርኛ ለማድረግ ዝግጅቱ ተጠናቋል፡፡ ኃላፊው እንዳሉት፣ በክልሉ የተማረ የሰው ኃይል ስላልነበረ ከ90 በመቶ በላይ የሚሆኑ የክልሉ የመንግሥት ሠራተኞች የሌላ ቋንቋ ተናጋሪ ነበሩ፡፡ በዚህም ምክንያት ክልሉ አማርኛን የሥራ ቋንቋ አድርጎ ለመጠቀም ተገዶ ቆይቷል፡፡
በአሁኑ ወቅትም የሌላ ቋንቋ ተናጋሪ ሠራተኞችን በአፋርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ሙሉ ለሙሉ ከመተካት ይልቅ፣ በየመሥርያ ቤቱ የአፋርኛ ቋንቋ አስተማሪዎቹን መድቦ አስተምሯል፡፡
አሁን በተያዘው አቅጣጫ መሠረት ሠራተኞች ሳይንሳፈፉ የክልሉ የሥራ ቋንቋን አፋርኛ ለማድረግ፣ ትምህርት ቤቶችም በአፋርኛ ቋንቋ እንዲያስተምሩ በቂ መምህራን ሲመደቡ የማስተማር ዝግጅቱም ተጠናቋል ብለዋል፡፡