ታየኝ እኮ፡ ሀረርና ወለጋ ገጥሞ፡ የ“ኦሮሚያ”ን ሪፐብሊክ ሲመሰርት ችግሩ ግን፡ ግንቦት ሰባትና እኛ ጋር ነው
ልጅ ተክሌ (ኦታዋ)
ብሄርንና ሀይማኖትን መሰረት ያደረገ ክርክር አስቸጋሪ ነው። ሀይማኖት ይብሳል። በንጽጽር፡ ከሀይማኖት ደግሞ ብሄር ለክርክር ይቀላል። ለጥቂት ጽንፈኛ ኦሮሞዎች የምንወረውረው ትችት ወይንም ስላቅ፡ አያሌ ለስላሳ ኢትዮጵያዊ ኦሮሞዎችን ሊያስቀይም ይሆንብናል። በመርህ ደረጃ፡ ከማናቸውም ብሄር-ቀመስ ድርጅቶች ጋር የሚደረግ ውይይት ባያስደነግጠኝም፡ መጀመሪያ ይሄ የግንባር/ህብረት ምስረታ ጉዳይ፡ ለጥቆ ደግሞ ከኦነግና ኦብነግ ጋር የሚደረገውን ውይይት ያመጣው ግንቦት ሰባት ነውና፡ ማምጣትም ብቻ አይደለም፡ የተወሰኑ የኦነግ አባላት የሚናገሩትን ሰባራ አረፍተ ነገሮች ይዞ፡ በግነት “ኦነግ የመገንጠል ሀሳቡን ጥሏል” ብሎ ለነገር ያሰፈሰፉትን በባዶ ሜዳ አስጮኋልና፡ መጀመሪያ ግንቦት ሰባትን ትንሽ ለኮፍ አደርገዋለሁ። ከዚያ ወደ ኦነግ እወርዳለሁ።