ወንድሙን ‹ጨርቃም› ብሎ የሚሳደብ…በይነጋል በላቸው

በየትኛው ምዕራፍና ቁጥር መሆኑ ለጊዜው ተሰወጠብኝ እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ በወንድማችን ላይ መፍረድ ወይም ወንድማችንን መሳደብ እንደማይገባን ለማሳሰብ ‹ ወንድሙን ጨርቃም ብሎ የሚሳደብ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል› የሚል ወይም ወደዚህ የሚቀርብ ማስጠንቀቂያ እንዳለው የቤተ ክህነት ዳራ ያለው ሰው ማስታወስ አያቅተውም፡፡ ጥሩ ትምህርታዊ ማሳሰቢያ ነው፡፡ አሁንም በየትኛው ምዕራፍና ቁጥር እንደተገለጸ አልከሰትልኝ አለ እንጂ ‹በራስህ ዐይን ያለውን ዕርፍ እሚያህል ጉድፍ ሳታወጣ በሰው ዐይን ውስጥ የሚገኝን ስንጥር እምታህል ጉድፍ ለማውጣት አትሞክር› የሚል ለአስተዋይ ሰው አጥንትን ሰርስሮ የሚገባ ማስገንዘቢያ አለ፡፡ ምን ይሄ ብቻ? አለላችሁ እንጂ ደግሞ በሰው ላይ ‹አትፍረድ ይፈረድብሃል!› የሚል ትልቅዬ – የሰማይ ስባሪ እሚያህል ግድንግድ ማስጠንቀቂያ – በዚያው አንባቢ ሳይሆን አገናዛቢ ጠቢብ አጥቶ የጆሮና የዐይን ያለህ እያለ የሚገኝ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፡፡

ዳር ዳርታየን የጠረጠረ ሰው መቼም አይጠፋም፡፡ መጠርጠር ጥሩ ነው፡፡ አዎ፤ ጠርጣሪ ለጠረጠረው የጥርጣሬ መነሻ የሚሆነው መጠራጠሪያ ምክንያት የሰሞኑ የኦነግና የግንቦት ሰባት የአሜሪካ ጉባኤ ቢሆን ቅዋሜ የለኝም፡፡ እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱብኝና የሰሞኑ የተቃውሞው ጎራ የነገር ውሽንፍር በፍጹም አላማረኝም፡፡ በዚህ መልክ የትም መድረስ አይቻልም ብቻ ሳይሆን ለወያኔ ድንጋይ እንደማቀበልም ሆኖ ታይቶኛል – ምን እኔን ብቻ ብዙዎቻችንን ቁልጭ ብሎ ታይቶናልም ማለት ይቻላል፡፡ ያገሬ ባላገር ሲተርት – ለተረት ደግሞ ማን ብሎት – ‹እህሉ አንድ ዓይነት ሴቱ አሥራ ሁለት› ይላል፡፡ ትክክል ነው፡፡ ኢትዮጵያ አንድ ናት – ለነገሬ ማጣፈጫነት አንድ ናት ልበል እንጂ ‹እንደሪያሊቲውማ› – (እንደውነቱማ ለማለት ነው) – ሀገር ምድሩ በጉራማይሌ ሲጥለቀለቅ እኔስ ለምን ይቅርብኝ – እናም እንደውነቱማ ሀገራችን ዕድሜ ለወያኔ በሃሊዮ በገቢር በይፋ ከተበታተነች እነሆ ሃያ ዓመቷን ባለፈው ግም ቦት ወር ውስጥ አስቆጠረች፡፡ በጣም በተለይ ከዚያን ጊዜ አንስቶ በመካከላችን ተዙሮ የተጣለብን ደንቃራና ቦረንትቻ ያንበሶ ገብስማ ዶሮ ይሁን የጨንገር ግንባረ ቦቃ በግ እርስ በርስ እያናቆረና እያቆራቆሰ ይሄውና ዛሬ በሃያኛው ዓመታችን እንኳን በሥልጣንና በቡድናዊ ስሜት ተለክፈን ከገባንበት የራስ ወዳድነት ወጌሻ ያልተገኘለት አዙሪት ልንወጣ አልተቻለንም፡፡ እጅግ በጣም ያሳዝናል፡፡ በዚህ አጉል ልክፍት ተጠምደን ከሀገርና ከሕዝብ ጥቅምና ፍላጎት ይልቅ በድርጅታዊና በፓርቲያዊ ጠባብ የፖለቲካ ምህዋር እንደዐይነ ሥውር ውሻ ወይ ድመት እዚያው በዚያው ስንድሞነሞን ብዙዎቻችን በሰውነት ተመልሰን የማናገኘውን ዕድሜያችንንና ወርቃማ ዕድላችንን በከንቱ እዬጨረስን ነን፡፡ የጥሩ ኢትዮጵያዊነት መለኪያና መለያ በጠባብ ቡድናዊ ስሜት ታውሮና በመጠላለፍ ፖለቲካ እስከወዲያኛው ተቀምብቦ መናቸፍ የሆነ ያህል በየጠፈጠፍናቸው ትንንሽ ግላዊ የዕብሪትና ትምክህት ዓለማት ውስጥ ከትመን በሕዝብ ስቃይና መከራ የምንደሰት በስቃይና መከራውም ለማትረፍ ሌት ከቀን ደፋ ቀና የምንል አስመሳዮች ዓለምን ጉድ እሰከምናሰኝ በዓለም ዙሪያ ሞልተናል፡፡ ይሄ ድርጊታችን የማይታወቅብን ይመስለናል እንጂ ታሪክና የመከራ ገፈት ቀማሹ ሕዝብ ጠንቅቀው እንደሚያውቁን መረዳት ይኖርብናል፡፡ ይህ አጠቃላይ አስተያየቴ ነው፡፡ ያለበት ይግነንበት ይባላልና የምለው ነገር በቀጥታም ይሁን በዘወርዋራ የሚነካው ካለ አዶከብሬውን ያስነካው፡፡ ማጭበርበር በአለማጭበርበር የሚተካበት፤ ቅዠትና ህልም በእውን የሚመነዘርበት፣ አንፋሽ አጎንባሽነት በሃቀኛ ዜጎች የምር አግለጋይነት የሚተካበት ዘመን መምጣቱ ስለማይቀር የታዘብነውን ካለማበል በመመሥከር የማተባችንን ቃል ኪዳን እንወጣ፤ ደግሞም ላበቃላት ዓለም፡፡

ታዲያም ይልቁናስ እንዲህ እናድርግ፡፡ ሁላችንም እንተዋወቃለን፡፡ ተቃዋሚዎቻችንን እናውቃቸዋለን፡፡ ወያኔንም እናውቀዋለን፡፡ የአቅምና የዘመን ፍርጃ ጉዳይ ሆኖ እንጂ የማንንም ማንነት ሁሉም ያውቃል፡፡ ስለዚህ ትዝብት ለማትረፍ ባንጣደፍ ደግ ነው፡፡ እናም ራሳችንን አድነን ከዚያም ለወገናችን ለመድረስ አሁኑኑ ፖለቲካዊ ንስሃ እንግባ፡፡ የበግ ለምድ ለብሰን በበጎች ጋጣ ውስጥ የገባን የተኩላና ቀበሮ ዝርያዎች ባፋጣኝ ሚናችንን እንለይ፡፡ ውሎ አድሮ ከዚህ የተሻለ ጥሩ አጋጣሚ ላናገኝ እንችላለን፡፡ እርግጥ ነው ብዙዎች ዕኩይ ዜጎቻችንን ዕድሜ ለ97 ምርጫና ከዚያም ወዲህ ለተከሰቱ አንዳንድ ማኅበረኢኮኖሚያዊ መድረኮች በቅጡ ለይተን አውቀናቸው እፎይ ብለናል፡፡ እነገሌ ማለቱ ከጨዋነት አንጻር ሆን ብዬ ተውኩት እንጂ እዚህ ላይ ልደቱንና ሞሼ ነው ማን ነው እሚባለውን ለአብነት ያህል ለመጥቀስ ቃጥቶኝ ነበር፡፡ ምን አሳጣኝ ብዬ ስም ልጥቀስ ወገኖቼ – ጊዜው ሲደርስና ትንቢቱ ሲፈጸም በስም ብቻ ሳይሆን የከሃዲው መዓት ከየጉራንጉሩ እየወጣ የየመክሊቱን ያገኝ የለም? ‹ተዐቀብ ዘንተ በአቢይ ትጋህ› ይላል መጽሐፉ፡፡

የሰሞኑን የኦነግና የግንቦት ሰባት ጉባኤ አስመልክቶ ብዙ እየተባለ ነው፡፡ በአወንታዊም በአሉታዊም፡፡ አንዳንድ ተግባራዊ እርምጃዎች እንደፍየል ሥጋ ናቸው፤ እንደ‹የጌዮርጊስን መገበሪያ መብላት›ም ሊባሉ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ ወያኔ አንዳች ነገር ሲያደርግ በተቃውሞው ጎራ አለን የምንል እውነተኛ ተቃዋሚዎችም አስመሳዮችም እንንጫጫለን፡፡ የሰሞኑ የወያኔ ድርጊት የእግር እሳት ሆኖብን የምናደርገውን አጥተን እንደተልባ እየተንጫጫን እንደምንገኘው ማለት ነው- እመለስበታለሁ፡፡ ተቃዋሚዎችም አንዳች ነገር ሲያደርጉ በወያኔ መንደር ሽበርና ሁከት ይነሳና ኢቲቪና መሰሎቹ የማያዥጎደጉዱት የፈጠራ ፕሮፓጋንዳ አይኖርም፡፡ በወያኔው ቤተ ሙከራ የተፈበረኩ ጉድ የሚያሰኙ ዶኩመንተሪ ፊልሞች ይለቀቃሉ፡፡ ለዚሁ ሥራ የተዘጋጁ ‹የተቃዋሚ›ና የነጻው ፕረስ አባላት ፈንጂ አጥምደው ቤተ መንግሥቱን በማፈንዳት በ‹ሕዝብ› ይሁንታ የቆመውን ሕገ መንግሥት በሽበርና በአመጽ ሊንዱ ሲሞክሩ ዕጅ ከፍንጅ በደኅንነትና ፀጥታ ኃይላት እንደተደረሰባቸው የሚያሳይ የሆሊውድንና የቦሊውድን ፊልሞች የሚያስንቅ ሸዋዚነገራዊ የፊልም ቅንብር ያለ አንዳች ሀፍረት ሊለቀቅ ይችላል፤ በዚህ ረገድ ከሃያ ዓመት በላይ የዘለቀ የዳበረ ልምድ ስላለን የወያኔን ኮኬነትና ልባውልቅነት ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ አልዋጥልን ያለውና ዝንተ ዓለማችንን እያሳፈረን የሚገኘው በተቃዋሚዎች አካባቢ ያለው አድሮ ቃሪያነት ነው፡፡ ‹ጨህን፤ ጮህን፤ እንዳልጮህን ተቆጠርን› ይላል አንዱ ግዕዛዊ ብሂል – ‹ነባይነ፤ ነባይነ፤ ከምዘባይነ ኮነ› ይሉታል ግዕዛውያኑ ሊቃውንት፡፡ ስለሚያዋጣን መንገድ ብዙዎች ብዙ ብለዋል፡፡ ነገር ግን የሰማቸው የለም፡፡ ጩኸታቸው የቁራ ጩኸት ሆኖ ነው የቀረው፡፡ በዚህም ምክንያት ወዲህ ስናይ ጨለማ፤ ወዲያ ማዶ ስናይ ጨለማ፤ ወደላይ ስናማትር ድቅድቅ ያለ ጨለማ፤ ወደታች ስንመለከት ጥቅጥቅ ያለ ጨለማ ሆኖብን ለጊዜው መውጫ ቀዳዳ አጥተናል፡፡ ወደየት እንመልከት? በሕዝብ ሥቃይና መከራ፤ ስደትና እንግልት የማያላግጥ ሁነኛ ሰው ከየት እናግኝ? ከግል ጥቅሙና ከበቀልና ጥላቻ ሱሱ የተላቀቀ ጤናማ ዜጋ ከየት ይምጣልን? የግል ፍላጎቱን በረድ አድርጎ ለብዙኃን ጥቅምና ፍላጎት የሚገዛ ትሁትና ጨዋ ታጋይ ከየት ይገኝ? በሁሉም አቅጣጫ ላም እሳት ወለደች ዓይነት ሆኖብን ልሣነ እንግልጣር ተናጋሪዎች ‹disillusionment› በሚሉት ዓይነት የህልም እልም ዓለም ውስጥ ተዘፍቀን እንገኛለን፡፡

ንጉሥ ዳዊት ‹ የሚያሰቃዩኝ እንዴት በዙ? ለምንስ እስከወዲያኛው ትተወኛለህ?› ብሎ በምሬት ወደ እግዚኣብሔር የጮኸው እንደኛ በቀቢጸ ተስፋ ቢከበብ ነው፡፡ ምን ያድርግ?

ግልጽነት ማንንም አይጎዳም፡፡ ኦነግና ግንቦት ሰባት ለኢትዮጵያ ችግር መፍትሔ አለን ብለው አንድነትም ሆነ ኅብረት መፍጠራቸው ከምንም በፊት በበጎ ገጽታው መታየት አለበት ባይ ነኝ፡፡ አይሳካላቸውም ይሳካላቸዋል ሌላ ጉዳይ ነው – እንደአካሄድ፡፡ ቢሳካላቸው እሰዬው፤ ካልተሳካላቸውም እሰዬው የሚያስብለን ኢትዮጵያዊ አንጀት ባይኖረንም – በኛ በጭቁኖች ጎራ ማንኛውንም የመፍትሔ ሃሳብና ውጤት ተኮር እርምጃ በጉጉት ለምንጠባበቀው ተስፈኞች ማለቴ ነው – ኪሣራን የለመድነው በመሆናችን እልፍ ሲልም መጀመር እንጂ መጨረስ የባህላችን አንዱ አካል ከመሆን ለጊዜው በመገታቱ ምክንያት ያን ያህል ማቅ የሚያስለብሰን እንግዳ ክስተት አይሆንብንም – ክፉኛ ማሳዘኑ ግን እንዳለ ሆኖ፤ ከኢዴኃቅ በፊትም ሆነ በኋላ ብዙ ተቦክተው ሳይጋገሩ ሾምጥረው የተጣሉ ወይም ተጋግረው ከምጣዱ ሳይወጡ ያረሩ ዳቦዎችን ስለምናስታውስ ዲባቶዎች ምሁራኑ የሚያንቀሳቅሱዋቸው ድርጅቶች ፎክረው በመቅረታቸው ምናልባት እነሱ ራሳቸው ትዝብት ውስጥ ይገቡ እንደሆነ እንጂ ያን ያህል ሙሾ እንደማያስወርዱ በበኩሌ ‹ግንዛቤ መውሰድ እችላለሁ› – በወያኔ አማርኛ አገላለጽ፡፡

እውነቱ ይሄ ሆኖ ሳለ በአንድ ወንድሜ ሰሞኑን የተጻፈውና በድረ ገጽ የተለቀቀው የሰባት ገጽ ወረቀት ደብዳቤ በመሠረተ ሃሳቡ ብስማማም በአቀራረቡ ግን ቅር እንደተሰኘሁ ሳልገልጽ ማለፌን አልወደድኩትም፡፡ እናም እኔም የምባለውን ልባል ብዬ የተሰማኝን ጻፍሁ፡፡

ትንሽ ዘና በሉ እባካችሁ፡፡ አለቃ ገብረ ሃና ባለቤታቸው ወይዘሮ ማዘንጊያ እንቅልፍ የያዛቸው መስለዋቸው ግገን ላይ ከተኛችው የቤታቸው ሠራተኛ ጋር ጋቢ ተጋፍፈው ይመለሳሉ፡፡ አጅሪት ማዘንጊያ ነቅተው ኖሮ አለቃ ሲመለሱ ጠብቀው ውሃ በማያሰኝ የወይራ ፍልጥ ወገብ ዛላቸውን ያነጉዱዋቸዋል፡፡ ያንን ዱላ ዋጥ አድርገው ችለው እንደተኙ ‹አንቺ፣ ማንን ነው እንዲህ በፍልጥ የምትነርቺው?› ብለው ይጠይቁዋቸዋል፡፡ አንጀታቸው ያረረው ማዘንጊያ፤‹ይሄን ልክስክስ ጥጃ ነዋ!› ይሉና በሾርኒ ይመልሳሉ፡፡ አለቃ ሆዬ ‹ እንዴ! ለቦና ጥጃ ታዲያ ውስ ምን አነሰው!› አሉዋቸው ይባላ – ድርቅ ለጎዳው ጥጃ፡፡ ‹ውስ› ለጥጃ የቃል ማስጠንቀቂያ መሆኑን ልብ ይሉዋል – ፍልጥ ለጥጃ ባይመከርም ከውስ በኋላ የሚመጣ ነው፡፡

ወያኔን ያህል ሚሊዮኖችን አጉራ ያስጠና የሀገርና የታሪክ ጠላት አራት ኪሎ ቤተ መንግሥት ላይ ተጎልቶ፣ ስደትና ሞት – ፖለቲካዊ እንግልትና ሥር የሰደደ ድህነት – በሽታና ማይምነት … ሀገራችንን እያንቀጠቀጧት እያሉ ተቃዋሚ ነን የምንል ወገኖች በረባ ባልረባው እርስ በርስ የምንጠማመደውና በነገር አኮርባጅ የምንሞሸላለቀው ምሥጢሩ ምን ይሆን? ብለን ብንጠይቅ ረብ የሚኖረው መልስ የምናገኝ አይመስለኝም፡፡ አንዳችን ለአንዳችን የምንወረውረው የአሽሙርና የአግቦ ናዳ የት ያደርሰናል? ለመሆኑ መሰዳደቡና መወራረፉ ይበልጥ ትግላችንን አጫጫው እንጂ በእስካሁኑ ሁኔታ ምን ጠቀመን? ብርሃኑን በስድብ አጥረግርጎ መለመላውን ማስቀረት ወያኔን ከአራት ኪሎ ቤተ መንግሥት በስንት ኢንች ወደውጪ እንዲያፈገፍግ ያደርገው ይሆን? ምንድነው እንዲህ አቅል ያሳጣን ጎበዝ? ብርሃኑስ ቢሆን ቢያንስ አሁን ከተቻለም መቼም ቢሆን ዲፕሎማሲያዊ የመሪ ቋንቋ ቢጠቀም ምን ይጎዳል? – እንደተባለው ጠያፍ ቃላትን ተጠቅሞ ከሆነ ማለቴ ነው፡፡ ምን ዓይነት ነገር ነው የተዞረብን? እስኪ ወደየኀሊናችን እንመለስና ራሳችንን እንመርምር፡፡ እንዲያው እንዲህ እንደጠፋን እንቅር? ጤናማ አእምሮ በማጣታችን እንደተበታተንንና የወያኔው ዘውጋዊ የምህንድስና ውጤት ሰለባዎች እንደሆንን ሩብ ምዕተ ዓመት ይሙላን?

ሁሉም ያልፋል፡፡ የማያልፈው ነገር – ከመቃብራችን በላይም በደማቅ ቀለም ተጽፎ ታሪካዊ ታዋሽነትን የማይነፍገን አሁን የምናተርፈው ሕዝባዊ የ‹ይህን አሉ› ትዝብትና ባልተገራ የዛር ፈረስ ላይ ተቆናጥጠን በምናደርገው ስሜታዊ የሽምጥ ግልቢያ አማካኝነት በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የምንሠራው የግፍ ሥራ ነው፡፡ መለስን ለምን እንደምንጠላ የምንረዳ ሰዎች ብርሃኑን ወይም ሌሎች ብርሃኑን መሰሎችን ለምን ልንወድ እንደቻልን እንዘነጋለን ተብሎ አይጠበቅም፡፡ የምወደውን ይበልጥ የምወደው የጠላሁትን እንዳይሆንብኝ ከመሳሳትና ከመመኘትም ጭምር እንደሆነ አፍታም ሊዘነጋብኝ አልፈልግም – በበኩሌ፡፡ አንዳችን ከአንዳችን ካልተማማርን ውሃ ቢወቅጡ እምቦጭ ዓይነት ነው – የዜሮ ድምር ይሉታል ፊደል የቆጠሩቱ – ፊደል በመቁጠራቸው ምን ያህል እንደተጠቀሙና ሌሎችን እንደጠቀሙ አለማወቄ ጥቂት ቢያስቆጨኝም፡፡ ስለዚህ ስንቅን በአህያ ዐመልን በጉያ እንደሚባለው – አይ ዐመልን በጉያ እንኩዋን አታምረኝም ተዋት – ከተደበቀች አንድ ቀን ትወጣለቻ – በሆደ ሰፊነት ተቻችለን በጋራ መታገል እንኩዋን ቢያቅተን በመከባበር ሳንጎዳዳ ለሀገራችን ነጻነት መጣር ነው የሚገባንና የሚያወጣንም፡፡ መናናቅና በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መነቁዋቆር ትግሉ ላይ በረዶ ውሃ ይከለብስበታል እንጂ እንደማይጠቅመን ሁላችንም አሳምረን የምናውቀው ነው፡፡ ይህን እያወቅን ደግሞ በኃይለ ቃልና በጠያፍ አነጋገር አንዳችን አንዳችንን እንዳንሸጥ እንዳንለውጥ አድርገን ሥራዬ ቤት ያሳደገውና ወግ ማዕረግ የጎደለው መደዴ ይመስል በገሃድ በነገር ወንጭፍ ብንተጋተግ ትርፉ ወያኔን ማስደሰትና በሕዝብ ቁስል እንጨት መስደድ ነው፡፡ ሌኒን እኮ ‹መማር፤ መማር፤ አሁንም መማር› ያለው ትምህርት በዕድሜ መግፋትም ሆነ በሀብት ክምችት የማይወሰን መሆኑን ለማጠየቅ ይመስለኛል፡፡ እናም አንጎላችንን ክፍት አድርገን በቀናን እንደማመጥ፡፡ እንደ መለስ ዜናዊ ወዳንጎል የሚወስዱ መንገዶችን ሁሉ በብረትና በአርማታ ጠርቅሞ ‹እንካስላንትያ በብጣሽ› ሲባሉ ‹ምናለ በድሪቶ› ማለቱ ወንዝ የማያሻግር መሆኑን ለመረዳት በምርጫም ይሆን በጡጫ በግድ አራት ኪሎ ቤተ መንገሥት መግባት አያስፈልግም፡፡ ለነገሩ ይቺ ቤተ መንግሥት እኮ የምትችለው አንድ ሰው ብቻ ነው! ለምንድን ይሆን ግን እኔም፣ አንተም፣ አንቺም፣ እሱም፣እሱዋም፣ እሳቸውም፣ እነዚያም፣ እነሱም፣እኚህኞቹም፣ እኒያኞቹም፣… ለዚች ጠባብና ብዙም የማትመች ቃላባይነትንም ይሁነኝ ብላ ለምታስተምር ወንበር የምንራኮተው? ወቸው ጉድ! የወንበር ቃል ኪዳን አይገርምም?

በአሁኑ ወቅት ወያኔ ነጋዴውን ማኅበረሰብ ቁም ስቅል እያሳየው ነው፡፡ በወር ሁለት መቶ ብር የማታስገባ ‹አርከበ ሱቅ› በዓመት አራትና አምስት ሺህ ብር ግብር ካልከፈላችሁ ተብለው አንዳንዶች ሊሰቀሉ ሲሉ በዘመድና ጉዋደኛ ሕይወታቸው የዛሬን ተርፎኣል፡፡ ጠቅላላ ወረቱ አምስት ሺህ ብር የማይሆን ነጋዴ የሚለው ስያሜ ሊሰጠው የማይበቃ ‹ነጋዴ› ባመት ስድስትና ሰባት ሺህ ግብር እንዲከፍል ሲጠየቅ ማየት በውነቱ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ ጠቅላላ የሱቁ ሸቀጥ ቢገመት ከሦስት መቶ ብር የማያልፍ ባለሱቅ ሁለት መቶ ሃምሳ ብር ከፍሎ የንግድ ፈቃድ እንዲያወጣና በየወሩም ከአንድ መቶ ብር በላይ ለመንግሥት እንዲያስገባ ይበየንበታል፡፡ በቀን ሠላሳ ብርና አርባ ብር ለማታስገባ ተራ ሱቅና ኪዮስክ ‹ካሽ ሬጂስተር› የተባለውን የወያኔ 666 የወጪ ገቢ መቆጣጠሪያ ማሽናዊ ቃፊር በ12500 ብር በግድ እንዲገዙ ወይም ንግዱን ዘግተው በረንዳ አዳሪ እንዲሆኑ እየተገደዱ ነው – ብዙዎች ወገኖቻችን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይ በአሁኑ ወቅት ፍርደ ገምድልነት እግር አውጥቶ በጠራራ ፀሐይ በየቦታው ሲራመድ ታገኙታላችሁ፡፡ ልታናግሩት ብትሞክሩ ግን አትችሉም – ትዕቢቱና ኩራቱ በዚያ ላይ ክርፋቱ አያስጠጉም፡፡ ማይምነትና የልቦና ድፍንነት ሲጋጠሙ የለየለት ድንቁርናና ዕብሪት ውስጥ ይዘፍቃሉ – እንዲህ እንደወያኔው ዘመን፡፡

ወያኔ የትምህርቱንም ዘርፍ በመዶሻ አናት አናቱን ብሎ እንደባብ ቀጥቅጦ ገድሎታል፡፡ በውጭ ሀገራት ያላችሁ ዜጎች በደንብ ተማሩና ቢያንስ ለሀገራችን የነገ ተስፋዋ ሁኗት እንጂ ሀገር ቤት ውስጥ ያለው ተማሪ አቡጊዳንም በቅጡ እንዳያውቅ ወያኔ አብዛኛውን ወጣት በሀሽሽና በልዩ ልዩ ሱሶች በመሸበብ አደድቦ ኮድኩዶታል፡፡ በዚያ ላይ ‹ዕንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ› እንዲሉ በግልም ሆነ በመንግሥት ኮሌጆች እንግሊዝኛ ቁዋንቁዋ በትምህርት መልክ እንዳይሰጥ ደንግጎ የማይም ተመራቂዎችን ቁጥር ለማብዛት ወያኔው ቆርጦ ተነስቶኣል፡፡ አንድ ተማሪ የዲግሪ ትምህርት መከታተልና በቀለም ትምህርት ወደላይ መዝለቅ እንዳይችልም ወደ አምስት እሚያህሉ ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጦ አንዱን ከባድ ፈተና ሲያልፍ ሌላ መሰናክል እንዲገጥመውና በእንዳያማህ ጥራው ዓይነት ሸረኛ መንግሥታዊ ሥልት(እንደመንደር መሠሪ) ታች ባለበት አነስተኛ የሙያ ሥልጠና ብቻ ተቀይዶ እንዲቀር ሁኔታዎች ተመቻችተዋል፡፡ አሥረኛን ያላለፈ ተማሪ ከቀናው በቲቬት ዲፕሎማ ይይዝና ሥራ ካገኘ ሁለት ዓመት ይሠራል፤ ከሁለት ዓመት በሁዋላ ሲኦሲ ለተባለ የሙያ ምዘና ፈተና ይቀመጣል፤ ያን ማለፍ ከቻለ እንደገና የኮሌጅ መግቢያ ፈተና ይወስድና ያን ሲያልፍ ለዲግሪ ገብቶ ይማራል- አሳሩ ብዙና ብዙ ነው፡፡ እንደሚባለው ከሆነ በአሁኑ ወቅት በተለይ የግል ኮሌጆች ወደመዘጋቱ ገደማ እያቀጣጩ እንደሆነ ውስጥ ውስጡን ይናፈሳል፡፡ ቀደም ሲል በርቀት ትምህርት፣ በሕግና በመምህራን ትምህርት ላይ የተጣለው ዕገዳም አሁንም እንደፀና ነው፡፡ ወያኔ ሁሉንም አሥሮና ቀፍድዶ ሚሊዮኖች በነፍስ ውጪ ነፍስ ግቢ የጭንቅና የጣር ሕይወት ውስጥ ነው የሚገኙት፡፡
ሀገርና ሕዝብ በዚህ የመከራ አዘቅት ውስጥ እየተንጠራወዙ በሚገኙበት ሁኔታ ውስጥ ነው እንግዲህ የደላቸው ሙቅ እያኘኩ አንዳንዶቻችንን በአግራሞት እያሳቁን ያሉት፡፡ በዚህ አጣብቂኝ ውስጥ እያለን ነው እንግዲህ ስለመገንጠልና ስለ የራስን ዕድል በራስ ስለመወሰን በየጉባኤው እዬተደሰኮረልን የሚገኘው፡፡ ዝንጀሮ ትሁን ጦጣ – ቀድሞ የመቀመጫየን ብላለች፡፡ አዎ፤ እውነትዋን ነው – እዬዬም ሲዳላ ነው መባሉም ለዚህ ነው፡፡ ቀድሞ ነገርስ ማን ነው ከማን የሚገነጠለው? ግራ እግሬ ከቀኜ ወይንስ ቀኝ እጄ ከግራየ? የአማራ አገር ቅርጽ ምን ይመስላል? የኦሮሞ አገር ቅርጽ ምን ይመስላል? እስኪ በየኅሊናችሁ አስቡዋቸው የሚገነጠሉትን አገሮች፡፡ ለምን ቀልዱ ሁሉ ወዝና ለከት እንዲኖረው አይደረግም? ዕብደት ለምን አይበቃንም? ከማይምነትና ከድህነት የተላቀቀ፣ ቢያንስ ከአድማስ ማዶ ሀገርና ሥልጣኔ መኖሩን የሚረዳ፣ ቁርሱን ቀምሶ ለራቱ የማይጨነቅ ሕዝብ ሲኖረን አይሻልም ስለሕዝበ ውሳኔና ስለ ነጻ ግዛት ምንነት ማውራት የሚኖርብን? በአንጻራዊ ሁኔታ የተሻለ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ሕይወት በሚመራባቸው ሀገርኛ ከተሞችና በአውሮፓና አሜሪካ እየኖርን በድሃ ሕዝባችን መቀለዱን ካልተውን ታሪክ ይፋረደናል፡፡ በቅድሚያ በነጻነትና በአስተዳደራዊ በደል መካከል ያለውን ልዩነት ለማወቅና ያን ለማጥፋት መጣር ብልህነት ነው፡፡ ሲዘፈን አጨብጫቢ የተገኘለት ዘፈን ሁሉ ቆንጆ ዘፈን ነው ማለት አይደለም፡፡ አንዳንዱ ሰውን ሆን ብሎ ገደል ለመስደድና በእግረ መንገድም የራሱን ድብቅ ዓላማ ከግቡ ለማድረስ የውሸቱን እያጨበጨበ ሰውን ችግር ውስጥ የሚከት አለ፡፡ ውሻ በማይጠራ ድምጽ ለተዘፈነ ዘፈን ተብዬ ቱሪማንቱሪ ዕጁ እስኪገነጠል የሚያጨበጭብና የሚያጋግል አለ፡፡ ዘመኑ የትንግርት በመሆኑ ለገደል ማሚቶም የሚያጨበጭብ አይጠፋምና ከስሜት አምባላይና አማላይ ፈረስ ወርደን ቢመረንም ቢጎመዝዘንም የእውነትን ጭራ እንያዝ፡፡ ያኔ መኖር እንጀምራለን፡፡ መኖር ስንጀምር ያኔ ሀገር ትወለዳለች፡፡ ሀገር ስትወለድ ያኔ ስደት ወደ ኢትዮጵያ ይሆናል፡፡ ስደት ወደ ኢትዮጵያ ሲሆን ያኔ የትንቢቱ ፍጻሜ ይሆንና ሀገራችን እውነተኛዋ የዳቦ ቅርጫት ትሆናለች – ‹የአንድ ማሣ ሰብልና የአንድ ላም ወተትም ለብዙዎች ይበቃል›፡፡… ለማንኛውም እስኪነጋ ናፈቀኝ፤ ጨለማው የፈለገውን ያህል ድቅድቅ ይምሰል እንጂ መንጋቱ ደግሞ አይቀርም፡፡ በኔ ይሁንባችሁ – ይነጋል፡፡

[email protected]