ኢሕአፓ (ዴሞክራሲያዊ) ስድስተኛ ጉባዔውን አካሄደ
የኢትዮጵያዊ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ዴሞክራሲያዊ) ከሰኔ ፳፫ እስከ ሰኔ ፳፯ ፪ ሺህ ፬ ዓ. ም (June 30 to July 4, 2012) ድረስ ከተለያዩ ክፍለ ዓለማት የመጡ አባላቱ የተሳተፉበት ስድስተኛ ጉባዔውን አካሂዶ በተሳካ ሁኔታ አጠናቀቀ።
ጉባዔው የድርጅቱን የአመራር ምክር ቤት እና የአባላት መብት አስጠባቂ ኮሚሽንን የሥራ ዘገባዎች አዳምጦ ከመረመረ በኋላ አጽድቋል። የኢትዮጵያን እና የዓለምአቀፍ ሁኔታዎችን ጉባዔው በጥልቅ ከመረመረ በኋላም፣ የህወሓት/ኢህአዴግ አምባገነናዊ ቡድን የግፍ አገዛዙን በአፈናና በሽብር ደግፎ ለማቆየት ከምንም ጊዜ በላይ በከፋ መልኩ በሀገሪቱ ዜጎች ላይ አሰቃቂ ግፍ እየፈጸመ እንዳለ ግንዛቤ ወስዷል። የመጻፍ፣ የመናገር፣ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሠልፍ የመውጣትና ሌሎች መሠረታዊ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች የተገደቡበት፣ ከፖለቲካ ጋር በተያያዘ ግድያና እስራት፣ ማንገላታትና ማሰቃየት፣ ማፈናቀልና ማሰደድ የአገዛዙ የየዕለት ተግባራት የሆኑበት፣ በሙስና በተጨማለቀና ብልሹ በሆነ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ሳቢያ ዜጎች ለከፍተኛ ሥራ አጥነትና ለችጋር የተጋለጡበት፣ ገበሬው ከእርሻ መሬቱ በልማት ስም የሚፈናቀልበት፣ የሀገሪቱ ለም መሬቶች ለውጭ ከበርቴዎች የሚቸበቸቡበት፣ የሀገሪቱ ድንበር እየተቆረሰ በስጦታ መልክ ለጎረቤት ሀገር የሚሰጥበት አስከፊ ሁኔታ ላይ ሀገሪቱ መውደቋን ጉባዔው በከፍተኛ ቁጭት አስተውሏል። ጉባዔው እነዚህንና ሌሎች ተዛማጅ ሁኔታዎችን ከመረመረ በኋላ አሁን በሀገራችን ላይ የተንሰራፋው የህወሓት/ኢህአዴግ አምባገነናዊ የአፈናና የጭቆና አገዛዝ በፖለቲካ፤ በኤኮኖሚና በማኅበራዊ ዘርፎች በሕዝባችን ላይ ያደረሰውንና እያደረሰ ያለውን በደል በጥብቅ አውግዟል። በሚከተሉት ዓበይት ወቅታዊ ጉዳዮችም ላይ ውሳኔዎችን አስተላልፏል።
ጉባዔው አገዛዙ በተቃዋሚ ኃይል መሪዎችና አባላት፤ በጋዜጠኞችና በንፁሃን ዜጎች ላይ በሽብርተኛነት ስም እየወሰደ ያለውን የመብት አፈና፣ እሥራትና እንግልት እያወገዘ፣ የታሠሩትን ሁሉ ለማስፈታትና የግፍ ሰንሰለቱን ለመበጠስ ትግሉን አስተባብሮና አጠንክሮ ለመታገል ወስኗል።
ከግንቦት ፱ ቀን እስከ ግንቦት ፲፪ ቀን ፪ ሺህ ፬ ዓ. ም (May 18 – May 21, 2012) ድረስ በኦታዋ ከተማ (ካናዳ) የተቃዋሚ ኃይሎች ጉባዔ ተካሂዶ ለተመሠረተው ሸንጎ ሙሉ ድጋፉን ሰጥቷል። የኅብረት ትግሉንም የበለጠ ለማጠናከር እንዲቻል አዲስ የተመረጠው የድርጅቱ አመራር አስፈላጊውን ሁሉ እንዲያደርግ መመሪያ ሰጥቷል።
የህወሓት/ኢህአዴግ አምባገነናዊ አገዛዝ የእስልምና ሃይማኖትን የውስጥ አስተዳደር ለመቆጣጠር የሚያደርገውን ጣልቃገብነት ጉባዔው እያወገዘ፤ የሃይማኖቱ ተከታዮች ለመብታቸው መከበር የሚያደርጉትን ትግል ደግፏል።
በልማት ስም ታሪካዊ ገዳማትን ለማፍረስና መናንያንን መጠጊያ ለማሳጣት እየተደረገ ያለውን ሀገር አጥፊ እርምጃ ጉባዔው አውግዟል። በተጨማሪም በስደት ላይ ያለው ሕጋዊ ሲኖዶስ በዋሽንግቶን ዲሲ ተሰብስቦ ይህንን በተመለከተ ያስተላለፈውን ውሳኔ ጉባዔው አድንቆ ሙሉ ድጋፉንም ሰጥቷል።
ኢሕአፓ ለሁለት ከተከፈለ በኋላ ኢሕአፓ (ዴሞክራሲያዊ) ድርጅቱን መልሶ ለማዋሃድ በአምስተኛው ጉባዔ ላይ አንድ አቀራራቢ አካል አቋቁሞ ሲሠራ እንደቆየ ይታወሳል፤ ይህ አቀራራቢ ኮሚቴ ያቀረበውን ዘገባ ጉባዔው ከመረመረ በኋላ አካሉ የጀመረው ሥራ እንዲቀጥል ወስኗል።
ጉባዔው የድርጅቱን የፖለቲካ ፕሮግራምና የውስጥ መተዳደሪያ ሰነዶቹን በጥልቀት ከመረመረ በኋላ አስፈላጊ ማሻሻያዎችን አድርጓል።
ጉባዔው ለሚቀጥለው የሥራ ዘመን የሚያገለግሉ የድርጅቱን የአመራር ምክር ቤት አባላትን እና የአባላት መብት አስጠባቂ ኮሚሽን አባላትን መርጧል።
በመጨረሻም ህወሓት/ኢህአዴግ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የጫነውን የግፍ ቀንበር አሽቀንጥሮ ለመጣል ሁሉም የተቃዋሚ ኃይሎች ያላቸውን ጥቃቅን ልዩነት ወደ ጎን በመተው የተባበረ ትግል እንዲያደርጉ ጉባዔው አጽንዖት በመስጠት ጥሪ አድርጓል። በተለይም ባለፉት አራት አሥርተ-ዓመታት በሀገራችን የተካሄዱትን የፓለቲካ ትግሎች ታሪክ ጉባዔው ከመረመረ በኋላ በተለያዩ የፓለቲካ ድርጅቶችና ኃይሎች ውስጥ የተፈጠረውን የፓለቲካ ልዩነት በአግባቡ ለመያዝ አለመቻሉ ሀገራችንን ለመታደግ በሚደረገው የጋራ የፓለቲካ ትግል ደንቃራ መሆኑንና ለአምባገነኖች መፈራረቅ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረ ጉባዔው ተገንዝቧል። ሀገራችንን ለማዳን፤ ፍትህ እንዲሰፍን፤ ዴሞክራሲና የሕግ የበላይነት እንዲከበሩ በአሁኑ ሰዓት ለሕዝባችን ፍትህና ዴሞክራሲ ለማምጣት ከሚታገሉ ኃይሎች ጋር ለመተባበር ጉባዔው ቃል ገብቷል። በተጨማሪም የዓላማና የፕሮግራም ተመሳሳይነትና አንድነት ካላቸው ድርጅቶች ጋር ከኅብረትም ዘለቅ ብሎ እንዲሄድ ጉባዔው ወስኖአል። የጉባዔው ተሳታፊዎችም እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩት ውሳኔዎች ለማሳካት ቃልኪዳናቸውን በማደስ ጉባዔው በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል።
ሀገራችንን ለማዳን እንተባበር!
ኢትዮጵያ በነፃነት ለዘላለም ትኑር!
(Phone: 301-578-4466; Fax: 301-449-8363; Email Address: [email protected])