በዱባይ አሰሪዋን እና ልጇን የገደለችው ኢትዮጵያዊት ሞት ተፈረደባት!

ወዳጄ ኢዮብ ብርሃነ፤ “አንዲት ኢትዮጵያዊት ሞት ተፈረደባት” የሚል መረጃ አድርሶኝ ነበር። ከዚሁም ጋር “ካላመንከኝ እህቷን ደውለህ ማናገር ትችላለህ!” ብሎ የስልክ ቁጥሯንም አስቀምጦልኛል። እኔም የፈጀውን ይፍጅ ብዬ ደወልኩላት…

እርሷም ይህንን አረጋገጠችልኝ…!

ሰናይት ትባለለች። በዱባይ “አባደና” ሰፈር በቤት ሰራተኝነት ተቀጥራ ትሰራ ነበር።  በምትሰራበትም ቤት አሰሪዋ የምታደርስባትን ጥቃት ለመከላከል ስትል በወሰደችው ርምጃ ርጉዝ አስሪዋን ትገድላታለች። ከዛም ደም የነካ ልብሷን ስታቃጥል በቤት ውስጥ የነበረው የ2 ዓመት ህፃን በጭስ ታፍኖ ይሞታል።

ወድያውም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውላ ፍርድ ቤት የቀረበችው ሰናይት ፍርዷን ለሁለት አመታት ስትከታተል ቆይታ የሞት ፍርድ ተፈረደባት። ሰናይት በጠበቃዋ አመካኝነት “የሞት ፍርዱ ተገቢ አይደለም” ብላ ይግባኝ የጠየቀች ሲሆን ይግባኙም ድጋሚ ታይቶ በድጋሚም የሞት ፍርዱ ተበይኖባታል።

እህቷ እንደነገረችኝ ከሆነ “ከዚህ በኋላ ይግባኝ መጠየቅ አትችይም!” ተብላለች።

ወይ ጣጣችን…! ምን ማድረግ ይቻለን ይሆን? የእህቶቻችን ሰቆቃ ማብቂያው የት የሆን…!? በእውነቱ ይህንን ዜና ስፅፍ እየተሰማኝ ያለው ሀዘን ማቆሚያው መቼ ነው…? መቼ ነው ሀገራችን ለሁላችንም የምትበቃን…? መቼ ነው መሰደዳችን የሚቆመው? መቼ ነው…?