ግጥም እናዋጣ… (አቤ ቶኪቻው)

ኢናሳ የተባለው የኢትዮጵያ ቆላፊ እና ጠላፊ መስሪያ ቤት የግለሰቦችን ፌስ ቡክ ሳይቀር በመቆለፍ ስራ ተጠምዷል። በትላንትናው ዕለት በርካታ ብሎጎች ድጋሚ እንደተዘጉ ሰምተናል። መንግስቴ ፈርቷል… በእውኑ እንዲህ ያለው ፍርሃት “ተራሮችን ካንቀጠቀጠ ትውልድ” አይጠበቅም…

እኔን ጨምሮ ሌሎችም “ባለ ብሎጎች” አንዱ ቢዘጋ በሌላ መስኮት ወደ አገራቸን መግባታችን እና ከወዳጆቻችን ጋር መጨዋወታችን እንደሚቀጥል እርግጠኛ ነኝ። ስለዚህ የተዘጋው በር ሁሌም  መንኳኳቱ አይቀርም ማለት ነው። ታድያ በተንኳኳ ቁጥር መንግስት እየተነሳ ሲዘጋ መንግስቴን ስትራፖ እንዳይዘው ሰጋሁለት…!

የዛሬ ሃሳቤን  በግጥም ብገልፅ በደንብ ይወጣልኝ ነበር። ነገር ግን ብንደፋደፍ ብንደፋደፍ ጠብ ሊልኝ አልቻለም። ታድያ ከወዳጆቼ ጋር ለምን አናዋጣም ብዬ እንደዚህ ጀመርኩ፤

በአንኳኪ ብዛት ሰላም ከምታጣ

በርህን ክፈተው ያሻው ይግባ ይውጣ…

ይበሉ ወዳጄ አንድ አንድ ስንኝ ያዋጡ… ከዛ ዜማ አበጅተን እንዘፍናት ይሆናል።